Error
  • JUser: :_load: Unable to load user with ID: 62
Saturday, 26 November 2011 09:21

ሜሲ ከሮናልዶ ትንቅንቁ ቀጥሏል - ቫን ፒርሲ ከዳር ቆሟል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

በፊፋ የዓለም ኮከብ ተጨዋች ምርጫ ከቀረቡ 23 እጩዎች የአሸናፊነቱ ግምት ለሊዮኔል ሜሲ የተሰጠ ቢመስልም የቅርብ ተፎካካሪዎቹ የሪያል ማድሪዱ ክርስትያኖ ሮናልዶና ሌላው የባርሴሎና ተጨዋች ዣቪ ኸርናንዴዝ ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ከ3 ዓመት በፊት ዋይኔ ሩኒ በሜሲና ሮናልዶ የተወሰነውን የኮከብነት ትንቅንቅ ለማጥበብ መሞከሩ ሲታወስ በፊፋ ኮከብ ተጨዋች ምርጫ መታጨት ያልቻለው የአርሰናሉ ቫንፒርሲ ከዳር በመቆም እየተነፃፀራቸው ነው፡፡ ከሜሲ፤ ሮናልዶና ዣቪ ሌላ የ2011 ኮከብ ተጨዋች በመሆን የወርቅ ኳስ ለመሸለም ይችላል የተባለው ሌላ ተፎካካሪ ዲያጎ ፎርላን ነው፡፡ የዓለም ዋንጫ ኮከብ ተጨዋች ሆኖ የወርቅ ኳስ የተሸለመውና ከኡራጋይ ጋር የደቡብ አሜሪካ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው የአትሌቲኮ ማድሪዱ ዲያጎ ፎርላን ከፍተኛ ግምት እየተሰጠው ነው፡፡

በእጩዎቹ ዝርዝር ከቀረቡት 23 ተጨዋቾች በስፔኖቹ ሃያላን ክለቦች ባርሴሎና ሪያል ማድሪድ የሚጫወቱት ብዛት 13 መሆኑ ላሊጋውን በኮከቦች ስብስብ የተጠናከረ መሆኑን አረጋግጧል፡፡ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በማን ዩናይትዶቹ ሊውስ ናኒና ዋይኔ ሩኒ፤ በሊቨርፑሉ ሊውስ ስዋሬዝ እና በሲቲው ሰርጂዮ አጉዌሮ ተወክሏል፡፡ በክለብ ደረጃ በእጩዎች ዝርዝር 8 ተጨዋቾችን በማካተት ባርሴሎና ሲመራ ሌላው የላሊጋ ክለብ ሪያል ማድሪድ በ5 ተጨዋቾች ይከተላል፡፡ ከአውሮፓ ውጪ እጩ መሆን ከቻሉት የ19 ዓመቱ የሳንቶስ ክለብ ተጨዋች ፓብሎ ኔይማር ሲጠቀስ አፍሪካን የወከለው በአሁኑ ግዜ በዓመታዊ ደሞዙ አንደኛ የሆነውና ብዙም ለማይታወቀው የሩሲያው ክለብ አንዚ የሚጫወተው ሳሙኤል ኤቶ ነው፡፡
በሌላ በኩል በፊፋ የፑሽካሽ የምርጥ ጎል ሽልማት ከቀረቡ 10 እጩዎች መካከል የኤሲ ሚላኑ ኢብራሞቪች፣ የባርሴሎናው ሊዮኔል ሜሲ፣ የሳንቶሱ ፓብሎ ኔይማር፤ የማን ዩናይትዱ ዋይኒ ሩኔይ ይገኙበታል፡፡
ፊፋ ለ2011 የዓለም ኮከብ ተጨዋች ምርጫ የቀረቡ 23 እጩዎቹን ከ2 ሳምንት በፊት ሲያስታውቅ ለሽልማቱ የቀረቡት ብቸኛ ተፎካካሪዎች የተባሉት ሊዮኔል ሜሲ እና ክርስትያኖ ሮናልዶ ላለፉት 5 ዓመታት ይህን ትንቅንቅ ሲያሳዩ የቆዩ ናቸው፡፡ የሜሲና ሮናልዶ ትንቅንቅ በተለይ ባለፉት ሁለት ዓመታት እየተወሳሰበ የመጣ ሲሆን ለሚቀጥሉት 5 ዓመታትም የሚቀጥል ይመስላል፡፡ ሁለቱ ተጨዋቾች በኮከብ ተጨዋቾች ምርጫና በኮከብ ግብ አግቢነት የሽልማት ፉክከሮች አስገራሚ ተቀናቃኝነት ይዘዋል፡፡ በተለይ በጎል ማስቆጠር ክህሎታቸው ተስተካካይ አጥተዋል፡ በላሊጋው በየውድድር ዘመኑ በጎሎቻቸው አዳዲስ ክብረወሰኖች በማስመዝገብ፤ ልዩ ታሪኮች በመስራትና ሪኮርድ በማስመዝገብ ላይ ናቸው፡፡ የሜሲና የሮናልዶ የኮከብነት ፉክክር ማራዶና ፔሌ ከሚነፃፀሩበት ሁኔታ ልቆ ሄዷል፡፡
ሊዮኔል አንድሬየስ ሜሲ
24 ሚሊዮን የፌስ ቡክ ወዳጆች
ከ2008 እኤአ ጀምሮ በባርሴሎና 286 ጨዋታዎች 203 ጎሎች
በአርጀንቲና ብሄራዊ ቡድን 41 ጨዋታዎች 11 ጎሎች
በባርሴሎና ክለብ ብቻ 17 ትልልቅ ዋንጫዎች
በፊፋ የዓለም ኮከብ ተጨዋች 2 ጊዜ አሸናፊ በ2009 እና በ2010 እኤአ
ደሞዝ 8.1 ሚሊዮን ፓውንድ በዓመት
ባንድ ጨዋታ በአማካይ 1.56 ጎሎች
ክርስትያኖ ሮናልዶ ዶሳንቶስ አቪዬሮ
10 ሚሊዮን የፌስ ቡክ ወዳጆች
ከ2002 እኤአ ጀምሮ በሶስት ክለቦች 429 ጨዋታዎች 226 ጎሎች
በፖርቱጋል ብሄራዊ ቡድን 87 ጨዋታዎች 32 ጎሎች
በማንችስተር ዩናይትድ 8 በሪያል ማድሪድ 1 በአጠቃላይ 9 ትልልቅ ዋንጫዎች
የፊፋ የዓለም ኮከብ ተጨዋች 1 ጊዜ አሸናፊ በ2008 እኤአ
ደሞዝ 11 ሚሊዮን ፓውንድ በዓመት
ባንድ ጨዋታ በአማካይ 1.58 ጎሎች
ቫንፒርሲስ
ሮቢን ቫን ፒርሲ በውድድር ዘመኑ በ33 ጨዋታዎች ለአርሰናል ያገባቸው ጎሎች 30 ከደረሱ ወዲህ ከሊዮኔል ሜሲና ክርስትያኖ ሮናልዶ ጋር ይነፃጸር ጀምሯል፡፡ ሰሞኑን አርሰናል በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የጀርመኑን ዶርትመንድ 2ለ1 አሸንፎ ወደ ጥሎማለፍ ሲሸጋገር ሁለቱንም ጎሎች ያገባው ቫንፒርሲ በፊፋ የዓለም ኮከብ ተጨዋች ምርጫ ከቀረቡት እጩዎች ባይካተትም በውድድር ዘመኑ ከታዩ ምርጥ ተጨዋቾች እኩል አድናቆት እያገኘ ነው፡፡
‹አብረውኝ ከተጫወቱ አጥቂዎች ምርጡ ነው› በሚል ያደነቀው የቡድን አጋሩ ማይክል አርቴታ ሲሆን ‹ቀንና ሌት እግር ኳስን የሚያስብ ልዩ ሰው ነው፡፡› በሚል የክለቡ አሰልጣኝ አርሰን ቬንገር አሞካሽተውታል፡፡
ቫንፒርሲ ለአርሰናል መጫወት ከጀመረ 7ኛ ዓመቱን የያዘ ሲሆን በሁሉም ውድድሮች 250 ጨዋታዎች አድርጎ 114 ጎሎችን አስመዝግቧል፡፡ ከአርሰናል ጋር በ2004 እኤአ የኮሚኒቲ ሺልድ ዋንጫን እንዲሁም በ2005 እኤአ የኤፍኤ ካፕ ድል በማስመዝገብ ሁለት የዋንጫ ክብሮች ብቻ ያለው ቫንፒርሲ ዘንድሮ ከክለቡ ጋር የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ወይንም የፕሪሚዬር ሊግ ዋንጫን ማግኘት ፍላጎት ቢኖረው አይደንቅም፡፡በፕሪሚዬር ሊጉ ቫንፒርሲ በኮከብ ግብ አግቢነት ሊጨርስ እንደሚችል የሚሰነዘሩ ግምቶች ይህን የሚያሳካው ልማደኛው ጉዳት ካልገጠመው መሆኑን በመግለፅ ነው፡፡
ቫን ፒርሲ የግብ ቁጥር ከሜሲና ሮናልዶ ሲነፃፀር
41 ያደረጋቸው ጨዋታዎች ብዛት፤ ሜሲ 58፤ ሮናልዶ 51
38 ያገባቸው ጎሎች ብዛት፤ ሜሲ 53፤ሮናልዶ 50
0.93 በአንድ ጨዋታ በአማካይ የሚያገባው ጎል ተመን፤ ሜሲ 0.91፤ ሮናልዶ 0.98

 

Read 8202 times Last modified on Saturday, 26 November 2011 09:28