ላለፉት 20 ዓመታት በሂፕሆፕ ሙዚቃ ከፍተኛ ተወዳጅነት እና ስኬት ባገኘው ራፐር ናስ ስም ሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ ፌሎውሺፕ ማቋቋሙን አስታወቀ፡፡ በሂፕሆፕ ሙዚቃ ታሪክ ያላቸውና ነባራዊ ገፅታን በረቀቀ መንገድ የሚያንፀባርቁ ሃሳቦችን በብዛት በመስራት ክብርና ዝና የተቀዳጀው ናስ፤ በሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ ናስር ጆንስ ፌሎሺፕ ተቋቁሞለታል፡፡ ዌብ ዱ ቦይስ ኢንስቲትዩት እና ሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ የሂፕሆፕ ክምችት ፌሎሺፑን የሚያስተዳድሩ ሲሆን የሂፕሆፕ ሙዚቃ ባህል፤ በታሪክ እና በፈጠራ ሂደት የሚኖረውን ሚና ለማጎልበት በሚል እንዲሁም ከሂፕሆፕ ጋር የተገናኘ የኪነጥበብ ትምህርት ለሚወስዱ ተማሪዎች ድጋፍ እንደሚሰጥበት ታውቋል፡፡ በሙሉ ስሙ ናስር ቢን ኦሉ ዳራ ጆንስ ተብሎ የሚታወቀው ራፕሩ፤ ባለፈው ዓመት “ላይፍ ኢዝ ጉድ” በሚል መጠርያ 11ኛ አልበሙን ለገበያ ማብቃቱ ይታወሳል፡፡