Administrator

Administrator

Monday, 07 April 2014 16:00

33ኛው “ግጥም በጃዝ”

ረቡዕ ይካሄዳል
33ኛው የ“ግጥም በጃዝ” ምሽት የፊታችን ረቡዕ ከምሽቱ 11፡30 ጀምሮ በራስ ሆቴል አዳራሽ እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ ግጥሞች፣ ወጎችና ዲስኩር በሚቀርብበት ዝግጅት፤ አርቲስት ግሩም ዘነበ፣ ገጣሚ ምስራቅ ተረፈ፣ ምንተስኖት ማሞ፣ በረከት በላይነህ እና ሚሊቲ ኪሮስ ሥራዎቻቸውን ያቀርባሉ ተብሏል፡፡ የመግቢያው ዋጋ በነፍስወከፍ 50 ብር ነው።

በፊልም ባለሙያዋ መቅደስ በቀለ (ማክዳ) ደራሲነትና ዳይሬክተርነት ተሰርቶ በኤራሶል ፊልም ፕሮዳክሽን የሚቀርበው “ሊነጋ ሲል” የተሰኘ አዲስ ፊልም በቅርቡ ለእይታ ሊበቃ ነው፡፡ የፊልሙ ዘውድ ፍቅር ድራማ ሲሆን በ “ባለታክሲው” ፊልም ላይ በመሪ ተዋናይነት የተወነው ሚኪያስ መሐመድ፣ ታዋቂዋ ተዋናይት ማህደር አሰፋ፣ ቃል ኪዳን አበራ፣ ቢንያም በቀለና ሌሎች አንጋፋና ወጣት ተዋንያኖች ተውነውበታል፡፡ ፊልሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ 11 ወራት የፈጀ ሲሆን በሚያዝያ ወር በግል ሲኒማ ቤቶችና በብሔራዊ ትያትር እንደሚመረቅ ታውቋል፡፡

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተመራቂዎችና የዩቶፒያ ክለብ አባላት፤ በቢዝነስና በስራ ፈጠራ መስክ ለስኬት በማነሳሳት የሚታወቁ ሰዎችን በመጋበዝ አነቃቂ ፕሮግራም አዘጋጁ፡፡ ለአርብ መጋቢት 28 ልዩ ዝግጅት የተመረጠው ቦታ የዩኒቨርሲቲው የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሲሆን፣ ከዩኒቨርሲቲው አመራሮች በተጨማሪ የ“ባለራዕይ ቶክሾው” ባለቤት ዶ/ር ኢ/ር ሳሙኤል ዘሚካኤል እና ዶ/ር ወረታው በዛብህ እንዲሁም የሰንሻይን ኮንስትራክሽን ባለቤት አቶ ሳሙኤል ታፈሰ በእንግድነት ተጋብዘዋል፡፡ ውጤታማው የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ አቶ ሰውነት ቢሻው እንዲሁም ታዋቂ አርቲስቶች ግሩም ኤርሚያስ እና ሰለሞን ቦጋለ እንደተጋበዙም አዘጋጆቹ ገልፀው፤ ተማሪዎችን ለቢዝነስና ለስራ ፈጠራ በማነሳሳት መልካም ስነ-ምግባርን የሚያላብስ ዝግጅት ነው ብለዋል፡፡

በአንተነህ ግርማ ተፅፎ በኪሩቤል አስፋው ዳይሬክት የተደረገው ‹‹ፍቅር ሲመነዘር›› ፊልም ነገ በ11ሰዓት በሀርመኒ ሆቴል በቀይ ምንጣፍ ሥነ ሥርዓት ይመረቃል፡፡ የ1ሰዓት ከ42 ደቂቃ ርዝመት ያለው ‹‹ፍቅር ሲመነዘር››፤ ሮማንስ ኮሚዲ ፊልም ሲሆን፤ በነገው ዕለት በኤድናሞልና በሀርመኒ ሆቴል እንደሚመረቅ ካም ግሎባል ፒክቸርስ አስታውቋል፡፡ ኩባንያው ‹‹አማላዩ››፣ ‹‹ስውሩ ሰይፍ››፣ ‹‹በራሪ ልቦች››፣ ‹‹ሼፉ››፣ ‹‹ወደ ገደለው›› እና ‹‹አማረኝ›› የተባሉ ፊልሞችን ሰርቶ ለእይታ ማቅረቡ ይታወሳል፡፡

መርሴ ሐዘን ወ/ቂርቆስ “ትዝታዬ፤ ስለ ራሴ የማስታውሰው (1891-1923) በሚል ርዕስ የህይወት ታሪካቸውን የተረኩበት መጽሐፍ ላይ ነገ ውይይት ይካሄዳል፡፡ በብሔራዊ ቤተ-መጻሕፍትና ቤተ-መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ፣ ከቀኑ 8 ሰዓት አንባቢዎች እንዲገኙለት የግብዣ ጥሪውን ያስተላለፈው ሚዩዚክ ሜይዴይ፤ የውይይት መነሻ ሃሳብ በአቶ መኮንን ተገኝ እንደሚቀርብ ገልጿል፡፡”

በኤርትራዊው ሠዓሊ ሰለሞን ኣብርሓ የተዘጋጁ ሥዕሎች የሚቀርቡበት ያልታ የ“ዕይታ” የሥዕል አውደርዕይ ባለፈው ማክሰኞ በጣልያን የባህል ማዕከል የተከፈተ ሲሆን በነገው ዕለት እምደሚዘጋም ታውቋል፡፡ በኤርትራዊው ስደተኛ የተሳሉ በርካታ ሥእሎች የተካተቱበት አውደርዕይ ዓላማ “የኢትዮጵያ እና ኤርትራ ህዝቦችን በማቀራረብ ወደ አንድነት ለማምጣት የበኩሌን አስተዋፅኦ ለማበርከት ነው” ብሏል፤ ሰዓሊው፡፡ሠዓሊው ካሁን ቀደም በኤርትራ የደቀመሃሪ መንደፍራ እና ሳዋ ከተሞች ሽልማት ባስገኙለት የሥዕል ትርኢቶች አውደርዕዮች ለይ መሳተፉን ለማወቅ  ተችሏል፡፡

Monday, 07 April 2014 15:56

ህልመኛው ክንፈኛ

ከትከሻዬ ጫፍ ግራና ቀኝ ካለው፣
ጉቶ የመሳሰለ ብቅ ያለ መሰለኝ፣
ይኸ እንግዳ ነገር እጅጉን ገረመኝ፡፡
የህልም ነገር ሆኖ መች አድሮ መች ውሎ፣
አየሁታ ወዲያው ጉቶው ክንፍ አብቅሎ፡፡
ወደፊት ወድሬ ሁለቱን እጆቼ፣
እግሬን ወደ መሬት ወደታች ዘርግቼ፣
በእነዚህ ረጃጅም ሰፋፊ ክንፎቼ፣
ከፍ ከፍ ወደ ላይ፣
ወዲያ ወደ ሰማይ!
አየሩን ቀዝፌ፣
ሄድሁ ተንሳፍፌ፡፡
ዕድሜዬን በሙሉ መሬት ተጣብቄ፣
አንድ ሜትር እንኳ ከፍ ያላልሁ ርቄ፣
ይኸው አየሩ ላይ ቀጨሁት ዓለምን፣
ያከራርመውና ዕድሜ ይስጥልኝ ህልሜን፡፡
እያደር ግን ኋላ ስካነው መብረሩን፣
ልክ እንደ ጭልፊቷ ሽው እልም ማለቱን፣
ጅው ብዬ ወርጄ ልክ እንደ የሎሱ፣
ወይ እንደ ድራጎን ያየር ላይ ንጉሱ(ሡ)፣
ይመስለኛል ያሰብሁ ልመካ በክንፌ፣
ያሻኝኝ ለመውሰድ ከመሬት ጠልፌ፡፡
አንዳንዱን ክፉ ሰው ላጥ አደርገውና፣
አንጠልጥዬ ወደ ላይ ርቄ እወስደውና፣
እንደ ሥራው መጠን ከድንጋይ ዓለቱ፣
ከጥልቅ ውቅያኖስ አልያም ከጅረቱ፣
ለቅቄ ስተወው ላይመለስ ከቶ፣
እረካለሁ መሰል ሳየው ሲቀር ሞቶ፡፡
ደግሞም ሆዳሙን ሰው ብድግ አደርግና፣
ፊቱን ወደ መሬት ዘቅዝቄ አይና፣
እጥለው መስሎኛል ጭው ካለው መሬት፣
አራዊት አምባ ምድር ሰው ከማይኖርበት፡፡
ይኸ ባለጌውን አለብላቢት ምላስ፣
የባጡን የቆጡን ቀባጥሮ የሚላላስ፣
ሳያስበው ድንገት ሁለት እጁን ይዤ፣
ከሰዎች መካከል ይህን ሰው መዝዤ፣
ወደ ላይ ወስጄው እዚያ ላይ አምጥቄ፣
ያዝ ለቀቅ አድርጌው ነፍሱን አስጨንቄ፣
ለቅቄ ስተወው ከላይ ደመናው ጥግ፣
ወደ ታች ወረደ ሄደ ሲምዘገዘግ፡፡
የሞተ መሰለኝ ምላሱን ጎልጉሎ፣
ብረት ምሰሶ ላይ በልቡ ተተክሎ፡፡
ሃይ የሚል የሌለው ከልካይም ተቆጪ፣
እኔው ራሴ ሆኜ ፈራጅ ዳኛ ቀጪ፣
ክንፎቼ እንዳይረግፉ እየለመንሁ ዕድሜ፣
እየቀጣሁ አለሁ ባለጌውን በህልሜ፡፡
ደግሞስ ማን ደርሶብኝ እንዴት ተነክቼ፣
ሽው ነው ወደ ላይ እብስ በክንፎቼ፡፡
ይህን ህልም እያየሁ ሳልነሳ ካልጋ፣
ሌቱ በረዘመ ጨርሶ ባልነጋ፡፡
ምን እንደ ህልም አለ፣ ከቶ ሌላ የለም፤
ህልመኛው ክንፈኛ አድራጊ ፈጣሪ …
        የሆነበት ዓለም፡፡
ይዘቱም መጠኑም የተስተካከለ፣
እንደዚህ እንደኔው ያለመ ሰው ካለ፣
ወደኔ ብቅ በሉ ሰማችሁኝ ሰዎች?
በጉዳዩ እናውራ የሌት አላሚዎች፡፡
በዝርዝር እንንገር ይህንን ሁኔታ፣
ምስጢሩን ገላልጦ ህልም ለሚፈታ፡፡
    ከአምሳሉ ጌታሁን ደርሰህ
የካቲት 2006 ዓ.ም

Monday, 07 April 2014 15:55

የፍቺ ነገር!

በአሜሪካ
በፍቺ የሚጠናቀቁ ጋብቻዎች የሚቆዩበት አማካይ ጊዜ 8 ዓመት ነው፡፡
ሰዎች ፍቺ ከፈፀሙ በኋላ እንደገና ለማግባት በአማካይ ለሶስት ዓመት ይጠብቃሉ፡፡
ጥንዶች የመጀመሪያ ፍቺያቸውን የሚፈጽሙበት አማካይ ዕድሜ 30 ዓመት ነው፡፡
ወላጆቻችሁ ስኬታማ ትዳር የነበራቸው ከሆነ ለፍቺ የመጋለጥ ዕድላችሁ በ14 በመቶ ይቀንሳል
ከጋብቻ በፊት አብሮ መኖር የፍቺን ዕድል 40 በመቶ ይጨምራል፡፡
ኮሌጅ የተማራችሁ ከሆናችሁ፣ ለፍቺ የመጋለጥ ዕድላችሁ 13 በመቶ ይቀንሳል፡፡
ከአሜሪካ ህፃናት ገሚሱ የወላጆቻቸው ትዳር ሲፈርስ ይመለከታሉ፡፡ ከእነዚሁ ህፃናት ግማሽ ያህሉ የወላጆቻቸው ሁለተኛ ጋብቻ ሲፈርስም ያያሉ፡፡
ኦክላሆማ ከፍተኛ ፍቺ የሚፈፀምባት ግዛት ስትሆን ከግዛቷ ያገቡ አዋቂዎች መካከል 32 በመቶው ፍቺ ፈጽመዋል፡፡
ዛሬ በአሜሪካ ካሉ ህፃናት ውስጥ 43 በመቶው ያለአባት ነው የሚያድጉት፡፡

      የ17 ዓመቱ ፕሮፌሽናል እግር ኳስ ተጨዋች ጌድዮን ዘላለም በብሔራዊ ቡድን ደረጃ ለየትኛው አገር መጫወት እንደሚፈልግ ለመወሰን ቢያንስ እስከ 3 ዓመት ሊዘገይ እንደሚችል ዘገባዎች አመለከቱ፡፡ ጌድዮን ከወር በፊት በታላቁ የእንግሊዝ ክለብ አርሰናል እስከ ከ2017 ለመቆየት የኮንትራት ማራዘሚያ ውል የፈረመ ሲሆን ጀርመን፤ በወላጆቹ ዘር ግንድ ከኢትዮጵያ፤ በተወለደበት አገር ጀርመን እና ለስምንት ዓመታት በኖረበት አሜሪካ  በብሄራዊ ቡድን ደረጃ እንዲጫወት ይፈልጋል፡፡  በብሔራዊ ቡድናቸው እንዲጫወትላቸው በተለይ አሜሪካ እና ጀርመን በየአቅጣጫው ጥረት እያደረጉ መሆናቸውን ያወሱ ዘገባዎች፤ ከ2 ሳምንት በፊት ወጣቱ በጀርመን ሀ- 17 ቡድን እንዲሰለፍ የቀረበለትን ጥሪ ሳይቀበል ከቀረ በኋላ  ጉዳዩ ማነጋገር መጀመሩን ያወሳው የኢኤስፒኤን ነው፡፡ አንዳንድ የጀርመን ሚዲያዎች ጌድዮን በጀርመን ብሄራዊ ቡድን የሚጫወትበትን እድል ማበላሸቱ ለወደፊት የእግር ኳስ ህይወቱ መጥፎ ጠባሳ መሆኑን በማውሳት እንደ ባየር ሙኒክ አይነት ክለቦች ውስጥ ለመጫወት ያለውን ተስፋ እንደሚያደበዝዘው እየገለፁ ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ጌድዮን በጀርመን ሀ -17 ቡድን  እንዲሰለፍ የቀረበለትን ጥሪ ወደ ጐን ገሸሽ ማድረጉን ተከትሎ በርካታ የአሜሪካ ስፖርት ሚዲያዎች እና የብሄራዊ ቡድን ደጋፊዎች አጋጣሚውን ለመጠቀም ተሯሩጠዋል፡፡ እንደ ኢኤስፒኤን  ዘገባ ጌድዮን ዘላለም፤ አሜሪካዊ ዜግነቱን በአፋጣኝ አግኝቶ ከወራት በኋላ ብራዚል በምታስተናግደው 20ኛው ዓለም ዋንጫ  በሚሳተፈው የአሜሪካ ብሔራዊ ቡድን  እንዲካተት ፊርማ በማሰባሰብ  እና ለፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ግልፅ ደብዳቤ በማስገባት  ዘመቻ ማድረግ ቀጥለዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በኢትዮጵያ እግር ኳስ አፍቃሪዎች ከፍተኛ ድጋፍ እና ክትትል ባለው የእንግሊዙ ክለብ አርሰናል የሚጫወተው ጌድዮን ዘላለም ከዋልያዎቹ ጎን እንዲሰለፍ ከወራት በፊት ተፈጥሮ የነበረው ፍላጎት የተቀዛቀዘ መስሏል፡፡
ኢትዮጵያና የትዊተር ምልልሱ
ጌድዮን በአርሰናል ክለብ በታቀፈበት ወቅት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከ31 ዓመታት መራቅ በኋላ ደቡብ አፍሪካ ላይ በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ መሳተፍ ላይ ነበር፡፡ ከዚያም በኋላ ዋልያዎቹ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ የምድብ ማጣርያ ስኬታማ ጉዞ  ነበራቸው፡፡ በዚሁ ጊዜ ጌድዮን ዘላለም ወደ እናት አባቱ አገር ኢትዮጵያ መጥቶ  ለብሄራዊ ቡድን እንዲጫወት  ከስፖርት አፍቃሪው ጋር ፍላጐት ያሳዩ ግለሰቦች ነበሩ፡፡ እነሱም የቀድሞው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ቴዎድሮስ አድሃኖም ነበሩ፡፡
አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ስለወጣቱ የተናገሩት በጋዜጣዊ መግለጫዎች ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በመደገፍ የቅርብ ክትትል የሚያደርጉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ደግሞ የማህበረሰብ ድረገፆችን ተጠቅመዋል፡፡
ከወራት በፊት በዓለም ዋንጫ ጥሎ ማለፍ የመጀመርያ ጨዋታ ኢትዮጵያ ከናይጄርያ  አዲስ አበባ ላይ ሲጫወቱ  ጌድዮን ዘላለም በትዊተር ድረ-ገጹ ሁለት መልክቶችን በመፃፍ አስነብቦ እንደነበር ይታወሳል፡፡ በወቅቱ የመጀመርያው ጎል በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ሲመዘገብ ደስታውን ለመግለፅ “ጎልልልልልልልልል......” ብሎ በመፃፍ አስነበበ፤ ጨዋታዉ በናይጄርያ 2ለ1 አሸናፊነት ከተጠናቀቀ በኋላ ደግሞ “ ...አሁንም ኮርቻለሁ ” የሚል አስተያየቱን በማስፈር ለዋልያዎቹ ብቃት አድናቆቱን ሲገልፅ አገሩን በቅርብ ርቀት እንደሚከታተል አረጋግጦ ነበር፡፡
ይህንን ተከትሎም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቴዎድሮስ አድሀኖም ጌድዮን ዘላለም ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እንዲጫወት በትዊተር ድረገፃቸው መልዕክታቸውን በማስፈር ያደረጉት ማግባባት ትኩረት ስቦ ነበር፡፡ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ለጌድዮን ባደረሱት ፈጣን መልዕክት “ ሃይ ጌድዮን…. ያንተን ሃሳብ መስማቱ  ጥሩ ነው፡፡ በቶሎ ለኢትዮጵያ መጫወትህን ተስፋ አድረጋለሁ”  ብለዋል፡፡ ጌድዮን ዘላለም ለዚህ ምላሽ አልሰጠም፤ ከዚያን በኋላ ኢትዮጵያ ተጨዋቹን ወደ ብሄራዊ ቡድን ለመቀላቀል የነበራት ፍላጎት እንደተቀዛቀዘ ቀርቷል፡፡
ምላሽ የተነፈገው የጀርመን ጥሪ
የቀድሞው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ቴዎድሮስ አድሃኖም ለጌድዮን ዘላለም ወደ አገሩ መምጣት የነበራቸው ፍላጐት ለወር ያህል በይፋ ሲያነጋግር ሰንብቶ ለወጣቱ የጀርመን እግር ኳስ ፌደሬሽን ጥሪ ቀረበለት፤ በሀ-17  ቡድን በመካተት ከስፔን ጋር በሚደረገው የወዳጅነት ጨዋታ እንዲሳተፍ ነበር፡፡ በዜግነት ሁኔታው ላይ የሚፈጥረው ችግር ስላልነበር ጌድዮን ጥሪውን በመቀበል ተጫወተ፡፡
ከዚሀ የጨዋታ ልምድ ከ4 ወራት በኋላ ግን ሌላ ጥሪውን የጀርመን እግር ኳስ ፌደሬሽን አቀረበ፡፡ ከሁለት ሳምንት በፊት ማለት ነው፡፡ ጌድዮን ዘላለም በአውሮፓ ደረጃ በሚደረገው የሀ-17 አህጉራዊ የምድብ ማጣሪያ ጨዋታ በሚሳተፈው የጀርመን ሀ-17 ቡድን እንዲቀላቀል የቀረበ ጥያቄ ነበር፡፡ ይህን ጥሪ ግን ጌድዮን ሳይቀበለው ቀረ፡፡ በምን ምክንያት እንደሆነ በይፋ የታወቀ ነገር የለም፡፡ አንዳንድ መረጃዎች እንደገለፁት ግን ጌድዮን ዘላለም ጥሪውን በመቀበል በዚሁ አህጉራዊ ሻምፒዮና ላይ ለጀርመን ሀ-17 ቡድን  ተሰልፎ ቢጫወት ኖሮ በተለይ ለአሜሪካ ብሔራዊ ቡድን ዜግነቱን ቀይሮ በዓለም አቀፍ ውድድሮች መሳተፍ የሚችልበትን ሁኔታ ያበላሽ ነበር ብለዋል፡፡
የአሜሪካውያን የፊርማ ማሰባሰብ ዘመቻ
ጌድዮን ከ2 ሳምንት በፊት በጀርመን ሀ-17 ቡድን  የቀረበለትን ጥሪ ገሸሽ ማድረጉ ግን በአሜሪካ ያለውን ፍላጎት ቆስቁሶታል፡፡ የአሜሪካ ሚዲያዎችና ደጋፊዎች ለጌድዮን በአስቸኳይ ዜግነት ተሰጥቶት ለብሄራዊ ቡድን እንዲጫወት ሰፊ ዘመቻ ጀምረዋል። ጌድዮን ዘላለም ለ8 ዓመታት በአሜሪካ በመኖር በእግር ኳስ ልምምድና ጨዋታ በሶስት አማተር ክለቦች ልምድ ስለነበረው ፍላጎቱ እንዲጠናከር ምክንያት ሆኗል፡፡
ጌድዮን ዘላለም የአሜሪካ ዜግነት፤ የመኖርያ እና የስራ ፈቃዶች የሉትም፡፡ በአሜሪካ እግር ኳስ  ሰፊ ልምድ ነበረው፡፡ ግን መቼም ቢሆን በዚያ አገር ብሔራዊ ቡድን ተሰልፎ ለመጫወት እንደሚፈልግ የሚያመላክት አስተያየት የሰጠበት ሁኔታ አላጋጠመም፡፡  የእሱን ፍላጎት ባይሰሙም የአሜሪካ ሚዲያዎችና የብሄራዊ ቡድን ደጋፊዎች ዘመቻቸውን ፊርማ በማሰባሰብ እና ለፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ ይድረስ ብለው የፃፉት ግልፅ ደብዳቤ  እየጣሩ ናቸው፡፡ እነዚህ አካላት ጌድዮን ለአሜሪካ ብሄራዊ ቡድን እንዲሰለፍ ፅፈውታል የተባለው ደብዳቤ  ከዚህ በታች የቀረበው ነው፡፡
“አገራችንን በመምራት ያላችሁን ታላቅ ኃላፊነቱ እናከብራለን፡፡ በትህትና የምንጠይቀው ጌድዮን ዘላለም ለአሜሪካ ብሔራዊ ቡድን እንዲጫወት የሚቻለው ሁሉ እንዲደረግ ነው፡፡ የማይቻል ከሆነ የሌላ አገር ማልያ ይለብሳል - ምናልባትም የኮሚኒስቶችን”
የአሜሪካ  ሚዲያዎችና ብሄራዊ ቡድን ደጋፊዎች በዚህ ዘመቻቸው  ተስፋ የቆረጡ አይመስሉም፡፡ በጥቂት ሳምንታት ውስጥ የጌድዮን ዘላለም ጉዳይ እልባት አግኝቶ ወጣቱ  በብራዚል በሚደረገው 20ኛው ዓለም ዋንጫ ከብሄራዊ ቡድን ጋር እንዲሳተፍ ግፊት ማድረጋቸውን ቀጥለዋል። የወቅቱ የአሜሪካ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ የሆነው ጀርመናዊው የርገን ክሊስማን ይህን ፍላጎት በማጤን በተጨዋቹ ላይ የቅርብ ክትትል ማድረግ መጀመሩን ሰሞኑን የገለፀው ደግሞ የኢኤስፒኤን ዘገባ ነው፡፡
በመጨረሻስ የማንን ማልያ ይለብሳል?
የ17 ዓመቱን ጌድዮን ዘላለምን ወደ ብሄራዊ ቡድናቸው ለመቀላቀል ጀርመንና አሜሪካ ከፍተኛ ፍላጎታቸውን በማሳየት ያለፈውን አንድ አመት በትኩረት ተከታትለውታል፡፡ በኢትዮጵያ በኩል የነበረው ፍላጎት ከአራት ወራት በፊት በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ቴዎድሮስ አድናሆም እና በቀድሞው የዋልያዎቹ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ከተንፀባረቀ ወዲህ ብዙም እንቅስቃሴ  እየተስተዋለ አይደለም። በተለያዩ ድረገፆች ስለ ጌድዮን ዘላለም በቀረቡ መረጃዎች ወጣቱ የኢትዮጵያ እና የጀርመን ዜግነት እንዳለው ይጠቀሳል፡፡ ስለ አሜሪካዊ ዜግነቱ የሚገለፅ መረጃ ግን የለም፡፡ በእርግጥ ጌድዮን የሚፈልግ ከሆነ በጀርመን ፓስፖርቱ ላይ ተጨማሪ የዜግነት እና የስራ ፈቃድ በመያዝ በአሜሪካ ብሄራዊ ቡድን የመጫወት እድል አለው፡፡ በአንፃሩ ግን በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ለመጫወት ሁለት ዜግነት መያዝ አይፈቀድለትም፡፡ በኢትዮጵያ  ህግ መሰረት አንድ ሰው የሁለት አገራት ዜግነት እንዲኖረው አይፈቀድም፡፡
በአርሰናል ክለብ እስከ 2017 እኤአ የኮንትራቱን ማራዘሚያ ውል  ከወር በፊት የፈፀመው ጌድዮን ዘላለም አሁን ትኩረቱ በክለቡ መጫወት ብቻ እንጂ በብሄራዊ ቡድን ደረጃ የየትኛውን አገር ማልያ ለብሶ እንደሚጫወት መግለፅ እንደማይፈልግ ከአርሰናል ክለብ የቅርብ ምንጮች የተገኙ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ጌድዮን ዘላለም ዜግነቱን ሰጥቶ የሚጫወትበትን ብሄራዊ ቡድን ለመወሰን ቢያንስ 3 ቢበዛ 5 ዓመታት ሊዘገይ እንደሚችል ያወሱ መረጃዎች ወቅታዊ ፍላጎቱ በአርሰናል ክለብ ማደግ እና በአውሮፓ እግር ኳስ ከፍተኛ ልምድ ማካበት እንደሆነ ይገልፃሉ፡፡ ተጨዋቹ በብሄራዊ ቡድን ደረጃ ለመጫወት የሚያስብ ከሆነ በ2018 እኤአ ራሽያ ላይ እንዲሁም በ2022 እኤአ በኳታር የሚደረጉትን 21ኛው እና 22ኛው የዓለም ዋንጫዎች መጠበቅ ግድ እንደሚሆንም ያስገነዝባሉ፡፡

  • 100 ሜትር በ56 ሰከንድ በክራንቾቹ ሮጧል፡፡
  • ሪከርዱ ገና በጊነስ መዝገብ እውቅና በማግኘት አልሰፈረም፡፡
  • የዩሲያን ቦልት አድናቂ ነው፡፡ ሊያገኘውም ይፈልጋል፡፡
  • በጀርመን ለመኖር የጥገኝነት ጥያቄ አቅርቧል፡፡
  • ከዓመት በፊት ስለህይወት ውጣውረዱና ሪከርድ ስለማስመዝገብ  አላማው ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረገው ቃለምልልስ ተናግሮ ነበር፡፡

   ከሳምንት በፊት “ፋርዝ” በተባለችና በሰሜን በቫርያ በምትገኝ የጀርመን ከተማ የ32 ዓመቱ ታምሩ ፀጋዬ በክራንቾቹ 100 ሜትርን በ56 ሴኮንዶች  በመሮጥ ባስመዘገበው ልዩ የዓለም ሪከርድ አነጋጋሪ ሆኗል፡፡ ታዋቂው የእንግሊዝ ታብሎይድ ጋዜጣ ዴይልሜል በፃፈው ዘገባ  አካል ጉዳተኛው  ታምሩ ፀጋዬ በክራንቾቹ ተጠቅሞ 100 ሜትሩን በመሮጥ ያሳየው አስደናቂ ስፖርታዊ ብቃት ለመላው የሰው ልጆች ከፍተኛ የሞራል መነቃቃት የሚፈጥር ልዩ ስኬት ነው ብሎ አድንቆታል፡፡
የታምሩ ፀጋዬ  ልዩና አስገራሚ ሪከርድ በጊኒስ የሪከርዶች መዝገብ ገና አለመስፈሩን የዘገበው ጨምሮ የዘገበው ዴይሊ ሜል፤ በአጭር ጊዜ እውቅና ማግኘቱ እንደማይቀር ገልፆ፤ ሪከርዱን ያስመዘገበበት ትእይንት በአገሪቱ ብሄራዊ የቴሌቭዥን ጣቢያ ሽፋን ማግኘቱን አውስቷል፡፡ አካል ጉዳተኛ ሆኖ ለመንቀሳቀስ በሚጠቀምባቸው ክራንቾች አስገራሚና ልዩ ክብረወሰኖችን በማስመዝገብ የተሳካለትን እንግሊዛዊውን  ጆን ሳንድ ፎርድ የጠቀሰው የዴይሊ ሜል ዘገባ ታምሩ ለእነዚህ ክብረወሰኖች ተቀናቃኝ መሆን እንደሚችልም ጠቁሟል፡፡ እንግሊዛዊው አካል ጉዳተኛበክራንቾቹ በመታገዝ ሁለት የዓለም ክብረወሰኖችን በማሳካት በጊነስ የሪኮርዶች መዝገብ ሰፍሯል፡፡  ጆን ሳንድ ፎርድ  በ2009 እ.ኤ.አ ላይ የኪሊማንጀሮ ተራራን በ4 ቀናት ከ20 ሰዓታት እና ከ30 ደቂቃዎች የወጣ ሲሆን፤ በ2011 እ.ኤ.አ ላይ ደግሞ በለንደን ማራቶን በመሳተፍ 42.195 ኪ.ሜ ርቀትን በ6 ሰዓት ከ24 ደቂቃዎች ከ48 ሰኮንዶች ጨርሶ በእነዚህ ሁለት ልዩ ክብረወሰኖች በጊነስ የሪከርዶች መዝገብ ለመስፈር በቅቷል፡፡  ታምሩ ፀጋዬ በጀርመኗ ፋርዝ ከተማ ካስመዘገበው ልዩ የዓለም ሪከርድ በኋላ  “አንድ በአንድ ህልሞቼን እያሳካሁ ነኝ፡፡ በህይወቴ ብዙ ውጣውረዶችን አሳልፌያለሁ፤ አካል ጉዳተኛ ብሆንም ብዙ ነገር ማድረግ እችላለሁ። በስፖርታዊ ብቃቴ እና አስደናቂ ተሰጥኦዎቼ ሌሎችን ሪኮርዶችን በማስመዝገብ መላው ዓለምን ማስደነቅ እፈልጋለሁ” ብሏል፡፡  ለዓለማችን ፈጣን የአጭር ርቀት ሯጭ ዮሴያን ቦልተ ከፍተኛ አድናቆት እንዳለው መናገሩን የጠቀሰው የዴይል ሜል ዘገባ “ዮሲያን ቦልትን እንደተምሳሌት የምመለከተው ጀግና ነው፡፡ እኔም ምርጥ ስፖርተኛ ነኝ፡፡ እሱ በፈጣን እግሮቹ እንደተሳካለት በጠንካራ እጆቼ በክራንቾቼ በመሮጥ ሪከርድ አስመዝግቢያለሁ፡፡ የሰራሁትን ታሪክ ቢያይልኝና ባገኘውገኘውም ደስ ይለኛል” ብሎ መናገሩንም አውስቷል፡፡
በሌላ በኩል ታምሩ ፀጋዬ ባለፉት ጥቂት ወራት በመላው አውሮፓ ከሚታወቀው እና “ሲርኪዊ ዲ ሶሊል” ከተባለ የሰርከስ ቡድን ጋር  እየሰራ እንደሚገኝ ያመለከተው አንድ የጀርመን ሚዲያ፤ በተለያዩ የጀርመን ከተሞች በመዘዋወር ትርኢቶችን ማቅረቡን  እንደሚቀጥል ቢገልፅም ወደ አገሩ ለመመለስ ፍላጐት እንደሌለውና በጀርመን አገር ለመኖር የጥገኝነት ማመልከቻ ማስገባቱን ጎን ለጎን ዘግቧል፡፡
በአዲስ አድማስ ያደረገው ቃለምልልስ
ታምሩ ፀጋዬ ለአስራ አምስት ዓመት እግሮቹ መራመድ ስለማይችሉ እጁን እንደ እግር በመጠቀም እየተሳበ ነበር የሚጓዘው፡፡ እናትና አባቱ አግልለውታል፡፡ ከቤተሰብ፣ ከማህበረሰብና ከጓደኞች ብዙ ተፅዕኖ፣ ብዙ ንቀትና ጥላቻ ደርሶበታል፡፡ ማደርያ አጥቶ ጐዳና አድሯል፤ ሊስትሮነትም ሰርቷል፡፡ ግን ሁሌም ትልቅ ታሪክ የመስራት ሪከርድ የማስመዝገብ ህልም እንደነበረው ከዓመት በፊት የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ከሆነችው አበባየሁ ገበያው ጋር ባደረገው ቃለምምልስ ተናግሮ ነበር፡፡  ታምሩ በክራንች በመታገዝ መንቀሳቀስ የቻለበትን ከፍተኛ የቀዶ ጥገና ህክምና ያገኘው በአጋጣሚ ነው፡፡ “ተዓምር” ከሚመስል ህክምናው በኋላ በእግሩ መሄድ ጀመረና በ16 ዓመቱ አንደኛ ክፍል ገባ፡፡ እስከ ኮሌጅ ዘለቀ፡፡ ከዛም ወደ ስፖርት ገባ፡፡ ሪከርድ ለማስመዝገብ አለመ፡፡ ይህንንም ፊልም የሚመስለው አስገራሚ የህይወት ታሪኩን በወቅቱ ከጋዜጣው ጋር ባደረገው ቃለምልልስ በስፋት ሲያወጋ ሁሉንም የህይወት ተሞክሮውን በማጠቃለል ሲናገር ወደቅሁ፤ ተጋጋጥኩ፤ ግን ተሳካልኝ  ብሎ ነበር፡፡ ታምሩ ፀጋዬ ከሳምንት በፊት ካስመዘገበው ልዩ የዓለም ሪከርድ በኋላ ከዓመት በፊት ከአዲስ አድማስ ጋር ካደረገው ቃለምልልስ አንዳንድ ምላሾቹን ለትውስታ እንዲህ ይቀርባሉ፡፡
‹‹ስወለድ አፈጣጠሬ የሚያስደንቅ ስለነበረ ፈቃዱ ዘገዬ አሉኝ፡፡ “እሱ እንደፈቀደ፣ እንደፈጠረው የሚያደርገውን ያድርገው” ለማለት ይመስለኛል፡፡ ታምሩ የሚለው ግን የቆሎ ት/ቤት እያለሁ የወጣልኝ ስም ነው፡፡ ይሄም ተመሳሳይ ትርጉም አለው፡፡ ሁለቱም እግሮቼ ስወለድ ወደ ኋላ ተቆልምመው ነው የተወለድኩት፡፡ አካል ጉዳተኛ ሆኜ ማለት ነው፤… የተወለድኩት ከላሊበላ 60 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ባለች የገጠር ሰፈር (ምዢ ማርያም በምትባል ቦታ) ነው፡፡ እናቴ፤ አያቴ ቤት  በቤት ሠራተኝነት ታገለግል ነበር፡፡ እኔ የተረገዝኩት አባቴ ከእናቴ ጋር በነበረው የምስጢር ግንኙነት ነው፡፡ አባቴ ሊዳር ሁለት ወር ሲቀረው እኔ ተወለድኩ፡፡›› በማለት ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ የልጅነት ታሪኩን አጫውቷል፡፡
ስትወለድ በቤት ውስጥ የነበረው ስሜት እንዴት ነበር፤ ካደግህ በኋላ ስትሰማ ምን ስሜት ተፈጠረብህ በሚል ጥያቄ ቀርቦለት ነበር፡፡ ታምሩ ፀጋዬ ምላሹን ሲሰጥ‹‹ ለእናቴም ለእኔም መጥፎ እንደነበር ዛሬ ዛሬ እሰማለሁ፡፡ አካል ጉዳተኛ ሆኜ በመወለዴ የአባቴ ቤተሰቦች ‹‹ይሄ ልጅ ከእኛ ዘር አይደለም፤ ዘር አሰዳቢ ነው›› ይሉ ነበር፡፡ እናቴ መረራትና ጥላኝ ጠፋች፡፡  ለ3 ወር ብቻ ጡት አጥብታኝና ከተማ ገባች፡፡ ሴት አያቴ ደረቅ ጡቷን ታጠባኝ ነበር፡፡ እናቴ  ካደግሁ በኋላ አልፎ አልፎ ቤተሰብ ለመጠየቅ ትመጣ ነበር፡፡ እኔን ያሳደገኝ አያቴ ነው፡፡ እስከ አምስት አመቴ ድረስ ከቤት መውጣት አልችልም ነበር፡፡ አፈና ተደርጐብኝ ሳይሆን በቃ መራመድ አልችልም፡፡ እንደ እባብ ነበር የምሳበው፤ በእጄ እየተራመድኩ፣ እጄን እንደ እግር እየተጠቀምኩ ማለት ነው፡፡ ሰው ስለሚያገለኝ ብቻዬን አወራለሁ፤ ብቻዬን እጫወታለሁ፡፡ አያቴ ቄስ ትምህርት ቤት እንድማር ይፈልግ ነበር…ያኔ በየደብሩ ቄስ ትምህርት ቤት አለ፡፡ እኔ ግን ፍላጐቴ ጨዋታ ብቻ ነው፡፡ በእጄ እየተሳብኩ …በሩጫም እንኳን የሚቀድመኝ አልነበረም፡፡ አያቴ የትምህርት ፍላጐት እንደሌለኝ ሲረዳ ከብት ጠባቂ አደረገኝ፡፡›› በማለት ያሳለፈውን የህይወት ውጣውረድ ገልፆታል፡፡
እንዴት የስፖርት እንቅስቃሴዎችን ማድረግ እንደጀመረ ሲናገር ደግሞ ‹‹ብቻዬን፡፡ አንድ ጓደኛዬ ነበር፤ ያየኛል፤ አብሮኝም ይሰራል፡፡ የማልሞክረው ነገር የለም፡፡ ኦፕራሲዮን አድርጌ በክራንች ነበር የምሄደው፡፡ ስለዚህ ለምን ተዘቅዝቄ በክራንች በእጄ አልሄድም ብዬ ተነሳሁ፡፡ በኢንተርኔት ላይ እንደዚህ ዓይነት ሪከርድ ያስመዘገበ የለም፡፡ በዚህ መንገድ ለምን ራሴን አላወጣም ብዬ ጀመርኩ። ወደቅሁ፣ ተነሳሁ፣ ተጋጋጥኩ፡፡ አሁን ከመቶ ሜትር በላይ እሄዳለሁ፡፡ የሚፈለገው በአንድ ደቂቃ ውስጥ ምን ያህል ሜትር ይኬዳል የሚለው ነገር ነው።›› ብሎም ነበር፡፡  በዓለም ላይ እንደዚህ ዓይነት ጅምናስቲክ የሚሰራ እንዳለም ተጠይቆ ነበር፡፡ ‹‹የለም፡፡ ተዘቅዝቆ በክራንች ላይ በእጅ በመሄድ እኔ ብቻ ነኝ፡፡ ቆየሁና ለምን በክራንች ላይ ሆኜ ደረጃ አልወርድም አልኩና ልምምድ ጀመርኩ፡፡ በተደጋጋሚ ወደቅሁ፤ ተጋጋጥኩ ግን አደረግሁት።›› የሚል ምላሽ ሰጥቶ የነበረው ታምሩ ፀጋዬ በዚያው ቃለምልልስ ለማስመዝገብ ስላሰበው ሪኮርዱ ስኬታማነት ማብራርያ እንዲሰጥ ተደርጎም ነበር፡፡ ‹‹በአንድ ደቂቃ ከ76 ሜትር በላይ ተዘቅዝቆ በክራንች ላይ በእጅ በመሄድ ሶስት ድርጅቶች እውቅና ሰጥተውኛል፡፡ “ወርልድ ሪኮርድ አካዳሚ”፣ “ወርልድ ሪኮርድ ሴንተር”፣ እና “ወርልድ ኦቶራይዝ›› ናቸው፡፡ የእነዚህ ሪከርዶች ባለቤት ነኝ፡፡ ሁለቱ ሪከርዶች ያገኘሁት በክራንች በመሄድ ነው፡፡ የራሴን ስም አስጠርቼ አገሬን ማስጠራት ነበር የምፈልገው፡፡ ይሄው ተሳካልኝ፡፡ ጊነስ ወርልድ ሪከርድ በዚህ ወር እውቅና ይሰጠኛል፡፡›› ብሎ ነበር፡፡