Administrator

Administrator

ሀዋስ ፋሚሊ ፊልም፤ “የራስ አሽከር” የተሰኘ አዲስ የቤተሰብ ልብ ሰቃይ ፊልም በነገው እለት በ8,፣10 እና 12 እንደሚያስመርቅ አስታወቀ፡፡ በአዲስ አበባና በግል ሲኒማ ቤቶች የሚመረቀውን የ100 ደቂቃ ፊልም የፃፈው ዘካርያስ ካሳ ነው፡፡ ሰርቶ ለማጠናቀቅ ሃያ ዘጠኝ ወራት የፈጀው ፊልም፤ ቀረፃ የተከናወነው በአዲስ አበባ፣ በደብረዘይትና በደቡብ ክልል እንደሆነ ታውቋል፡፡ በፊልሙ ላይ ሽመልስ አበራ (ጆሮ)፣ ዝናህብዙ ፀጋዬ፣ ቶማስ ቶራ፣ ዳንኤል ሙሉነህ፣ እሱባለው ተስፋዬ፣ ትዕግስት ዋሲሁን፣ ወንድወሰን ብርሃኑ (ዶክሌ)፣ አንዱአለም ሽፈራው እና ሌሎችም ተውነዋል፡፡

ድምፃዊ ዮሴፍ ገብሬ (ጆሲ) አዲስ የቴሌቪዥን ቶክ ሾው ሊጀምር መሆኑን አስታወቀ፡፡ በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስ (EBS) የሚጀመረው የቴሌቪዥን ቶክ ሾው Jossy in z House የሚል ርእስ ያለው ሲሆን ዝግጅቱ በፋሽን እና ስነጥበብ ላይ ያተኩራል፡፡ የነገ ሳምንት በእለተ ትንሳኤ የሚጀመረው ዝግጅት ዘወትር እሁድ ምሽት ከሁለት ሰዓት ጀምሮ ለአንድ ሰዓት የሚታይ ሲሆን ሐሙስ ከምሽቱ 4 ሰዓት ይደገማል፡፡

በዶ/ር ግርማ ግዛው የተዘጋጁና በሥራ ፈጠራ ላይ ያተኮሩ ሁለት መፃህፍት በነገው እለት በፑሽኪን አዳራሽ ከረፋዱ 4 ሰዓት ላይ እንደሚመረቁ አዘጋጁ አስታወቁ፡፡ መፃህፍቱ፤ “ሥራ ፈጠራ፣ ጥቃቅን አነስተኛና መካከለኛ የንግድ ድርጅቶች በኢትዮጵያ ሕግ እይታ” እና “ሥራ ፈጠራ፣ ንግድ እና የንግድ ሥነምግባር” በሚሉ አርእስት የተፃፉ ናቸው፡፡

ሥነ ጽሑፍን፣ ነፃ የሀሳብ መንሸራሸርንና የንባብ ባሕልን በማጐልበት የሚንቀሳቀሰው ፔን ኢትዮጵያ፤ ሁለተኛውን የፀሐፍት ጉባዔ ዛሬ በጣሊያን የባሕል ማዕከል ሊያካሂድ ነው፡፡
የጉባኤው ጭብጥ “የትርጉም ሚና ለኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ እድገት” በሚል ሲሆን፤ ምሁራን ጥናታዊ ጽሑፎቻቸውን እንደሚያቀርቡና ውይይት እንደሚደረግባቸው ተገልጿል፡፡
በጉባኤው ላይ የፔን አባላት የሆኑ ገጣሚያን፣ ፀሐፊ ተውኔቶች፣ ልብወለድ ፀሐፊዎች፣ ጋዜጠኞችና ሌሎች የሥነ ጽሑፍና የሚዲያ ቤተሰቦች ታዳሚ ሲሆኑ የኖርዌይና የጣሊያን ፔን ፕሬዚዳንቶችን በእንግድነት ይገኛሉ፡፡

 

Saturday, 27 April 2013 11:51

የግጥም ጥግ

ገና ከጅምሩ
በቤት አራሥነት ሸክም … በአዲስ ኑሮ
አሐዱ ብዬ
የራስ ማስተዳደር ማተብ ሳጠልቅ … ከወላጅ እትብት
ተገንጥዬ
ሲሟሽ ሲሟሽ ሲታሰስ … ሲጋገር የመኖር እንጎቻዬ
በቆራስማ ማጥንት ታጥና … ማጠንሰስ ስትጀምር ገንቦዬ
ኑሮን አልፋ ብዬ ኑሮን በስመአብ ብዬ
ኑሮ ኪራራይሶን
ገና አንዲት ዶቃ ላማትብ ስቆጥር
ምነው ያደርገኛል እንደመፍዘዝ ነገር
እንደመቆናጠር
ተስፋን መቁረጥ አይሉት ወይ ተስፋን ማጠናከር
መበራታት አይሉት ወይ መደነጋገር
ብቻ የሆነ ስሜት ብቻ የሆነ ነገር
እኩል አይሉት ሠናይ ደስታ አይሉት ሥቃይ
ብቻ የሆነ ሥሜት ግልጽ ያልሆነ ጉዳይ

***

ሰሙ ዝቅ ወርቁ ርዝቅ
በቀመር ተሰልቶ፣
በዋጋ ተዋዝቶ፣
በሰም ቢታሸግም
ያለ ወርቅ እሺ አይልም፡፡
የዛሬ ጨረታ ኩሩ ነው ቀብራራ፤
ራሱን ይኮፍሳል፤
በታክቲክ ዝቅ ብሎ፣
በቴክኒክ ከፍ ይላል፡፡
(“ከጃርት ወደ ጃርት” ከሚለው
የካሣሁን ከበደ
የግጥሞች እና ወጐች መድበል የተወሰደ - 2000 ዓ.ም)

 

 

አንድ ብዙ አማካሪ ያላቸው ንጉሥ፤ ሁሉም ባለሟሎቻቸው በተሰበሰቡበት አንድ ጥያቄ ጠየቁ፡፡ “የመጀመሪያው ጥያቄዬ”፣ አሉ ንጉሡ፡፡ “ከዚህ እስከሰማይ ምን ያህል ርቀት እንዳለው የሚያውቅ ይንገረኝ?” አሉ፡፡ ሁለተኛው ጥያቄዬ፤ “እኔ ብሸጥ ምን ያህል የማወጣ ይመስላችኋል?” “አስበን እንምጣ ንጉሥ ሆይ!” ብለው ባለሟሎቹ ሄዱ፡፡ ከዚያም፤ አንደኛው - ኮከብ ቆጣሪዎችን እንጠይቅ አለ ሁለተኛው - ኮከብ ቆጣሪዎች ዕጣ - ፈንታ እንጂ ኪሎ ሜትር አያውቁም፡፡ ይልቅ ደብተራዎችን እንጥራና የሚደግሙትን ደግመው የሚገለጥላቸውን ይንገሩን፡፡ ሦስተኛው - ደብተራዎችም ቢሆኑ ስለአጋንንት ትብትብ መፍቻ፣ ስለመናፍስት እንቅስቃሴ እንጂ ስለምድር - ሰማይ ርቀት የሚደግሙት የላቸውም፡፡

አራተኛው - እንግዲያው አዋቂ እንጠይቅ አምስተኛው - ጠንቋይ ለራሱ አያውቅም ባካችሁ፤ ይህንን ያንን እያነሱና እየጣሉ ሲከራከሩ፤ ከአቅራቢያቸው የሚገኝ አንድ ደበሎ - ለባሽ ያዳምጣቸው ኖሮ፤ “አባቶቼ፤ ይሄ የምትነጋገሩበት ነገር እንዲህ የሚያሟግትና ሊቅና ደብተራ የሚያፋልግ ጉዳይ አይደለም” አላቸው፡፡ ይሄኔ አንደኛው፤ “ታዲያ ምን እናድርግ ትላለህ በእኛ ዕውቀት ደረጃ የምንፈታው ባይሆንልን እኮ ነው፡፡” የቆሎ ተማሪውም፤ “እኔ መልሱን ልሰጣቸው እችላለሁ፡፡ ንጉሡ ፊት አቅርቡኝ” አላቸው፡፡ አማካሪዎቹ ጥቂት ካቅማሙ በኋላ፤ በቃ እንውሰደውና ይናገር ብለው ተስማሙ፡፡ ንጉሡ ዘንድ ቀርበውም፤ “ንጉሥ ሆይ! ንጉሥ ለጠየቁት መልስ መስጠት እችላለሁ የሚል ሰው ይዘን መጥተናል” ንጉሥ - “ይቅረባ እንየው!” የቆሎ ተማሪው ሲቀርብ ንጉሡ ተገርመው፤ “ይሄ ደበሎ - ለባሽ ነው የረባ መልስ ይሰጣል ብላችሁ ያመናችሁት?” አንደኛው - “አዎ ንጉሥ ሆይ!” ንጉሥ - “ጥያቄዬ፤ ‘ከመሬት እስከ ሰማይ ምን ያህል ይርቃል? እኔ ብሸጥስ ምን ያህል አወጣለሁ?’ የሚል ነው፡፡

“ የቆሎ ተማሪውም፤ “ንጉሥ ሆይ! ከዚህ እስከ ሰማይ 1000 ኪ.ሜ ይሆናል፡፡ አይበለውና እርሶ ቢሸጡ 29 ብር ያወጣሉ፡፡” ንጉሥ - እኮ አስረዳና! ቆሎ ተማሪው - “ከመሬት እስከሰማይ ያለውን ለመለካት ስለማይችሉ ነው 1000 ኪ.ሜ ያልኩት 29 ብር ያልኩዎት ደግሞ እየሱስ የተሸጠው 30 ብር በመሆኑ ነው፡፡ እርሶ ከዚያ ያንሳሉ፡፡ ስለዚህም ቢያወጡ ቢያወጡ በአንድ ያንሳሉ ብዬ ነው፡፡ ንጉሡ በመልሱ ተደስተው፣ አመስግነው ሸለሙት፡፡ * * * ስመ-ጥር አማካሪዎች የማይሰነዝሩዋቸው፣ ተራ የሚመስሉ አስተዋይ ሰዎች ግን ሳይጠራጠሩ የሚሰጡት ፋይዳ ያለው አስተሳሰብ፤ አገር ያድናል፡፡ የበታች ሆነው ታስበው፣ ታላቅ ሃሳብ ሊያቀርቡ የሚችሉ ሰዎችን በፋኖስ መፈለግ ያስፈልጋል፡፡ ለመፈለግ ደግሞ “ከእኔ ውጪም ለአገር አሳቢ ሊኖር ይችላል” ብሎ ማመን ተገቢ ነው፡፡ “ትኬት አልገዛም፤ ዝም ብዬ ባቡሩ ላይ እሳፈራለሁ” በሚል ሚንግዌይ ስለድፍረት ነግሮናል። ወይ የባቡሩ ሸፍተራን ይታለላል፡፡

ወይ አይመጣም፡፡ ወይ እንደራደራለን። አለበለዚያ እወርዳለሁ፤ ብለን የምንጓዘው ጉዞ፤ ለግዴለሽ ዕቅድ - አልባነታችን መገለጫ ይሆነናል፡፡ ያለዕውቀት ባቡሩ ላይ መሳፈር ወይ የብልጠት፣ ወይ አይነቃብኝም ብሎ የማሰብ ወይም ሌላውን የመናቅ አሊያም ተደባልቆ የመጓዝ ሁኔታ፤ እነሆ ዛሬ ከዘመናት በኋላ ፈጣን ነው ባቡሩን እንድንዘፍን ያደርገናል፡፡ ሳርኮክ የተባለው ፈላስፋ፤ በፍልሚያ የሚያምኑ አካላት፤ በጦርነት ሌሎቹን ድል ካደረጉ በኋላ፤ ‘ጠላት ካጣን እርስ በርስ ይዋጣልና’ የሚል ደረጃ ይደርሳሉ” የሚለንን ልብ እንበል፡፡ ሁልጊዜ የአገሬ እድገት፤ በኪራይ ሰብሳቢዎች ላይ ያገኘሁት ድል ነው! ምርጫው ያለሳንካ በመካሄዱ ነው! ፀረ - ህዝብና ፀረ - ህገመንግሥት አመራሮችን በማስወገዳችን ነው! ወዘተ… ከሚለው ባሻገር፣ ከሣጥኑ ወጣ ብለን ለማሰብ እንሞክር፡፡

ችግሮችን ወደህዝብ ማድረስ የሀቀኛ ዜጐች ግዴታ ነው!! ሆኖም ያለንበት ሁኔታ አንድ ክስተትን አጉልቶ እያሳየን ነው፡- የታፈኑ የሚመስሉ ጉዳዮች ነበሩንን? የሚል፡፡ የጤናማ አመለካከት ጥያቄ ነው፡፡ በህዝብና በአገር ላይ ክፉ ድርጊት ሲፈፀም እርምጃ ሳይወስዱ እጁን አጣጥፎ መቀመጥ አደገኛ እንደሆነ ሁሉ፤ እርምጃንም በስሜታዊነት ወይም በመካር አሳሳቾች ግፊት ከመውሰድ መቆጠብ ያባት ነው! ሰሞኑን “መልካም አስተዳደር በዘመቻ የሚፈታ ችግር አይደለም” የተባለው አስገራሚ አረፍተነገርና ዕውነታ፤ “የጠፋው በግ ተገኘ” የሚያሰኝ ነው፡፡ መልካም አስተዳደር፣ በሙያ በበሳል - ጥበብ (wisdom)፣ የህዝብ ጥቅም - ተኮር በሆነ መልክ ይቃኝ፤ ተብሎ አያሌ ጊዜ ተነግሮ ዛሬ ይፋ መሆኑ አስደሳች ነው፡፡

ዘመቻ በየአቅጣጫው ሊፈተሽ ሊመረመር ይገባል - ለሀገርና ለህዝብ ጥቅም ሲባል፡፡ ነኒውሪን ቤቫን የተባለው ፖለቲከኛ ስለቸርችል እንደጻፈው፤ ከዓለም ጋር ያለ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት፣ የጐረቤት ሀገሮች ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት፣ እርስ በርስ ያለ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት፤ ሲላላ፤ በ20ኛው ክ/ዘመን ያለው ዲፕሎማት የ18ኛው ክ/ዘመን ቋንቋ የሚናገር ይሆናል፡፡ አስቸጋሪ ሁኔታ በገጠመው ቁጥር ግን “ተኳሽ - ጀልባ ላኩ” ከማለት አይቆጠብም! ይላል፡፡ ቀልብን ገዝቶ፣ አዕምሮን አትብቶ አገርን ማስተዋል የታላቅ መሪ ጥበብ ነው፡፡ መሪ፤ “ንፁህ ወርቅ እሳት አይፈራም!” የሚለውን አልሰማ ብሎ ከተዘናጋና እሳቱ እየበላው መሳቅ መጫወት ከሆነ ሥራው፤ ስለሀገራችን እርግጠኛ መሆን አንችልም፡፡ “ሸማኔ ውሃ ሲወስደው፣ እስካሁን አንድ እሰድ ነበር፤ አለ” ማለት ይሄው ነው!!

  • 1 የአቶ መለስ ዜናዊ ምትክ መሆናቸውን ለማስመስከር የሞከሩበት ነው ግዙፎቹ እቅዶች (ለምሳሌ የባቡር ፕሮጀክት) መጓተታቸውንና የገንዘብ ችግርን በሚመለከት፣ እንዲሁም በቤኒሻንጉል የተፈናቀሉ ሰዎች ዙሪያ ትችት አዘል ጥያቄ ቀርቦላቸዋል። ጠ/ሚ ኃይለማርያም ለፓርላማው የሰጡት ምላሽ፣ የአቶ መለስን ዘዴ የተከተለ ነው - “መንግስት ላይ በተሰነዘረው ትችት ላይ የባሰ ትችት የመጨመር ዘዴ”
  • 2. የማይሳካ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ አጣብቂኝ ሆኖባቸዋል ግዙፎቹ የግድብ፣ የባቡር፣ የኢንዱስትሪ. የኤክስፖርት እቅዶች፣ እንዲሁም የእህል ምርት ለማሳደግና ስራ አጥነትን ለማቃለል የወጡ እቅዶች የማይሳኩ መሆናቸውን ከምር አምነው ለመቀበል አልደፈሩም። እቅዶቹ “በተያዘላቸው ጊዜ እየተተገበሩ ናቸው” እያሉ በተደጋጋሚ ይናገራሉ። ግን ደግሞ “የመቀነስ አዝማሚያ ታይቷል” ይላሉ።

እውነት ለመናገር ኢህአዴግ በ”ስሜት” ተነሳስቶ በ2002 ዓ.ም መጨረሻ ላይ ያዘጋጀው “የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ” አልሳካ ያለው በጠ/ሚ ኃይለማርያም ደሳለኝ ድክመት አይደለም። እቅዱ እንደማይሳካ በተግባር የታየው በመጀመሪያው አመት በ2003 ዓ.ም ነው። አምና ደግሞ፤ የእቅዱ ውድቀት አፍጥጦ ወጣ። በዚህ በዚህ፣ አቶ ኃይለማርያም ከሌሎች የኢህአዴግ መሪዎች የተለየ ተጠያቂነት ሊጫንባቸው አይገባም። በአብዛኛው የመንግስት ፕሮጀክቶች በማስፋፋት የአገሪቱን ኢኮኖሚ በአምስት አመት ውስጥ በእጥፍ ለማሳደግ ታስቦ እቅድ መውጣቱ ነው ዋነኛው ጥፋት። በመንግስት ፕሮጀክቶችና ኮርፖሬሽኖች አማካኝነት አገር ሊያድግ እንደማይችል በደርግ ዘመን በደንብ ታይቷልኮ።

የኢህአዴግ “የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድም” ከውድቀት ሊያመልጥ የማይችለው፤ እንደ ደርግ እቅድ የግል ኢንቨስትመንትንና የግል ጥረትን የሚያጣጥ በመሆኑ ነው - በአጭሩ በአቶ ሃይለማርያም ድክመት አይደለም የኢህአዴግ እቅድ ሳይሳካ የሚቀረው። ይልቅስ፣ ጠ/ሚ ኃይለማርያምን ተጠያቂ የምናደርጋቸው፤ የአምስት አመቱ እቅድ እንደማይሳካ እየታወቀ፤ “እየተሳካ ነው፤ እንደታቀደው እየተሰራ ነው” ብለው ሊያድበሰብሱ ከሞከሩ ነው። በእርግጥ፤ እቅዱ እየተሳካ አለመሆኑን ሙሉ ለሙሉ አልካዱም። የእርሻ ምርት እንደታሰበው አላደገም ብለዋል። ኤክስፖርትም እንዲሁ።

“የጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት ምርታማነት”ም የተወራለት ያህል እንዳልሆነ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቅሰዋል። እንዲያም ሆኖ፤ እቅዱን አለመሳካት ሙሉ ለሙሉ ባይክዱም፤ ሙሉ ለሙሉም አምነው አልተቀበሉም። “የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅዱ”፤ ከሞላ ጎደል በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ እየተተገበረ እንደሆነ ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተደጋጋሚ የገለፁት። ለመሆኑ የትኛው እቅድ ነው፤ በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ እየተከናወነ የሚገኘው? ካሁን በፊት እንደጠቀስኩት፣ ትልቅ ትኩረት የተሰጠው የህዳሴ ግድብ ግንባታ እንኳ በእቅዱ መሰረት እየተከናወነ አይደለም። በጣም ተጓቷል። በአምስት አመት ውስጥ ግንባታው ይጠናቀቃል ነበር የተባለው። ግን በሁለት አመት ውስጥ የተከናወነው ስራ፣ 18 በመቶ ብቻ ነው። በዚህ ስሌትም፣ ግንባታው 11 አመት ሊፈጅ ይችላል። “የግልገል ጊቤ 3” ግንባታም እንዲሁ፤ በእቅዱ መሰረት ሊሄድ አልቻለም። በ1998 ዓ.ም የተጀመረው የግልገል ጊቤ 3 ሃይል ማመንጫ፣ የዛሬ ሁለት አመት ግንባታው ተጠናቅቆ ወደ ስራ እንዲገባ ታቅዶ ነበር። አልተሳካም።

እቅዱ ተከልሶ፣ የግንባታ ማጠናቀቂያ ጊዜው ወደ ዘንድሮ ተራዘመ። ግን እንኳን ዘንድሮ በሚቀጥለው አመትም አይጠናቀቅም። ግንባታው ገና 71% ላይ ነው። ቢያንስ ተጨማሪ ሶስት አመት ሳያስፈልገው አይቀርም። እናም በ2002 ዓ.ም ወደ ሁለት ሺ ሜጋ ዋት ገደማ የነበረው የኤሌክትሪክ ሃይል የማመንጨት አቅም፣ በ50 በመቶ እንዲያድግና ዘንድሮ ሶስት ሺ ሜጋ ዋት እንዲደርስ የወጣው እቅድ አልተሳካም። እዚያው ከነበረበት ደረጃ ፈቅ አላለም። ከሁሉም የላቀ ትኩረት የተሰጣቸው ግድቦች፣ በተያዘላቸው እቅድ ሊከናወኑ ካልቻሉ፣ ሌሎቹ እቅዶች ምን ያህል እንደሚጓተቱ አስቡት። በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ላይ የተጠቀሱት ግዙፍ የሳሙናና የወረቀት ፋብሪካዎችም ድምፃቸው የለም። ዋነኛ የእድገት መሰረት ይሆናሉ ተብለው በመንግስት በጀት የተመደበላቸው አነስተኛና ጥቃቅን አምራች ተቋማትስ? ከቁጥር የሚገባ ለውጥ አልተመዘገበም። ፈፅሞ የእድገት ምልክት አልታየባቸውም። እንዲያውም፣ ከሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች ጋር ሲነፃፀሩ፣ አነስተኛና ጥቃቅን አምራች ተቋማት ወደ ኋላ እየቀሩ መሆናቸውን የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። ለነገሩ፣ በኢህአዴግ ጉባኤ ላይም በግልፅ ተጠቅሷል።

የአምናው የእርሻ ምርት እድገትም እንዲሁ የእቅዱን ግማሽ አያክልም። በአማካይ በነፍስ ወከፍ ስሌት፣ የእርሻ ምርት በ6 በመቶ እንዲያድግ ቢታቀድም፣ በተግባር ግን ከ2.5 በመቶ ያለፈ እድገት አልተገኘም። ብዙ የተወራላቸው አዳዲስ 10 የስኳር ፋብሪካዎችም ገና ብቅ አላሉም። ከ8 አመት በፊት የተጀመሩ ነባር የስኳር ፋብሪካ ፕሮጀክቶች እንኳ፣ በወጉ ሊጠናቀቁ አልቻሉም። የስኳር ምርት በሶስት እጥፍ አድጎ ዘንድሮ 10 ሚሊዮን ኩንታል ገደማ ይደርሳል ተብሎ ነበር - በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ። እህስ? የዛሬ አራት አመት ከነበረበት ደረጃ ትንሽ እንኳ ፎቀቅ አላለም። እንዲያውም ወደ ታች ወርዷል፤ ከ3 ሚሊዮን ኩንታል በታች ሆኗል። ከአገር ውስጥ ፍጆታ የሚበልጥ ስኳር ተመርቶ፣ ዘንድሮ በኤክስፖርት ወደ ሁለት ቢሊዮን ብር ገደማ ገቢ ይገኝበታል ተብሎ ነበር። ጠብ ያለ ነገር የለም። እንዲያውም የአገር ውስጥ ፍጆታን ለማሟላት ከውጭ ስኳር ለማስመጣት በቢሊዮን የሚቆጠር ብር ወጪ ተደርጓል። ባቡርስ? የባቡር ነገርማ ከሌሎችም የባሰ ሆኗል። የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ላይ እንደተጠቀሰው ቢሆን ኖሮ፤ አገሪቱ ዘንድሮ 1700 ኪሎሜትር የባቡር ሃዲድና የባቡር ትራንስፖርት ይኖራት ነበር። ቢያንስ ቢያንስ የጂቡቲ መስመር ተሰርቶ አገልግሎት መስጠት ይጀምር ነበር። ግን እንደ እቅዱ አልሆነም። እስካሁን የተሰራው ሃዲድ “የ650 ኪሎሜትር 15%” ነው ተብሏል።

ቢበዛ ከመቶ ኪሎሜትር አይበልጥም ማለት ነው። የጂቡቲ መስመር ሁለተኛው ደግሞ ገና የአፈር ቁፋሮ ላይ ነው። ወደ ሰሜን ወደ ምዕራብ አቅጣጫ የተባሉት የባቡር መስመሮችማ ገና ዲዛይናቸው አላለቀም። የኮንዶሚኒዬም ቤት ግንባታም ተመሳሳይ ነው። ስለ ኮንዶሚኒዬም ብዙ ብዙ እቅዶች ሲዘረዘሩና በሪፖርት ሲቀርቡ አይገርማችሁም? በየአመቱ 50ሺ ኮንዶሚኒዬም ቤቶች ይገነባሉ ሲባል ትዝ ይላችኋል - በ97 ዓም። አንድ ሶስተኛውን እንኳ ማሟላት አልተቻለም። በእድገትና ትራንስፎርሜሽ እቅድ ላይ፣ አመታዊው የግንባታ መጠን ወደ 30ሺ ዝቅ እንዲል ተደረገ - በሶስት አመት 90ሺ መሆኑ ነው። ይሄም አልተቻለም። በሶስት አመት ውስጥ ለነዋሪዎች የደረሱ አዳዲስ የቤት ግንባታዎች ሲቆጠሩ፣ በአመት ከአስር ሺ አይበልጡም - የእቅዱ 30 በመቶ እንደማለት ነው። ጠቅላላ የኢኮኖሚውን አዝማሚያ በግልፅ የሚያሳይ ሌላ መረጃ ከፈለጋችሁ፤ በኤክስፖርት የሚገኘውን ገቢ መመልከት ትችላላችሁ። የእድገትና የትራንፎርሜሽን እቅድ የተዘጋጀው፤ በ2002 ዓ.ም ከሸቀጦች ኤክስፖርት 2 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ከተገኘ በኋላ ነው።

አምስት አመት ውስጥ በአራት እጥፍ አድጎ 8 ቢሊዮን ዶላር እንዲደርስ ታስቦ በወጣው እቅድ መሰረት፣ ዘንድሮ ወደ 5 ቢሊዮን ዶላር ገደማ የኤክስፖርት ገቢ መገኘት ነበረበት። ግን ሊሆን አይችልም። ለዚህም ነው እቅዱ ተከልሶ፣ በዚህ አመት ከኤክስፖርት 3.7 ሚሊዮን ዶላር ለማግኘት የታቀደው። ይሄም አልተሳካም። በስምንት ወራት ውስጥ የተገኘው የኤክስፖርት ገቢ 2 ቢሊዮን ዶላር ብቻ ነው። በአመቱ መጨረሻ ቢበዛ ቢበዛ 3 ቢሊዮን ዶላር ሊደርስ ይችላል። የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅዱ ፈፅሞ ሊሳካ እንደማይችል ሁነኛ ማረጋገጫ የሚሆንብን፣ ይሄው የኤክስፖርት ገቢ ዝቅተኛነት ነው። ለምን ቢሉ፤ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ አገኛለሁ በሚል ሃሳብ መንግስት ያቀዳቸው በርካታ ፕሮጀክቶች ተግባራዊ ሊሆኑ አይችሉም። በትምህርትና በስልጠና በኩልስ፣ እቅዱ እየተሳካ ነው? ቃላትን ማንበብ የማይችሉ ተማሪዎች ምን ያህል ብዙ እንደሆኑ የተለያዩ ጥናቶችን በማጣቀስ መልስ መስጠት ይቻላል። ግን፣ በኢትዮጵያ ሬድዮ የተሰራጨ አንድ ዜና ብቻ በመስማት የአገሪቱን የትምህርት ሁኔታ አዝማሚያውን መገመት የሚቻል ይመስለኛል።

የቴክኒክ ኮሌጅ ውስጥ ከወዳደቁ እቃዎች መበየጃ ተሰራ የሚል ነው የዜናው ርዕስ። በኢትዮጵያ ሬድዮ የምንሰማቸው ዜናዎች “አስገራሚ” አይደሉ? ረቡዕ ማታ ሁለት ሰዓት ላይ፣ የእለቱ ሁለተኛ ትልቅ ዜና፣ በጅጅጋ የቴክኒክ ኮሌጅ፣ ከወዳደቁ ነገሮች መበየጃ እንደተሰራ ይገልፃል። በየጉራንጉሩ የሚዘጋጀውን መበየጃ፣ ለአንድ የቴክኒክ ኮሌጅ እንደ ትልቅ ስራ መቆጠር የጀመረው ከመቼ ወዲህ ይሆን? ግርድፍ “ትራንስፎርመር” እንደማለትኮ ነው። ከመበየጃ ጋር ሲነፃፀር፣ የሞባይል ቻርጀር እጅግ የተራቀቀ “ትራንስፎርመር” ነው። የኮሌጁ አስተማሪዎችና ተማሪዎች፣ መበየጃ ለመስራት መጣራቸው ስህተት ባይሆንም፣ መበየጃው “ከወዳደቁ ነገሮች” የተሰራው ኮሌጁ ምን አይነት ቢሆን ነው? መበየጃ ለመስራት የሚያስችል ቁሳቁስ ከሌለው፣ እንደ ሞተርና ጄነሬተር የመሳሰሉ ነገሮችን ለማደስማ ጨርሶ አይታሰብም ማለት ነው። የቴክኒክ ኮሌጅ እንዲህ ነው? ካስታወሳችሁ፣ የረቡዕ ማታ የመጀመሪያ ዜና፣ ጠ/ሚ ኃይለማርያም ለፓርላማ ያቀረቡትን ሪፖርት የሚመለከት ነበር። ለኢንዱስትሪ ምርትና ልማት ከፍተኛ ትኩረት እንደተሰጠው የገለፁት ጠ/ሚ ኃይለማርያም፣ ለቴክኒክ ትምህርት ስለሚመደበው በጀትና ስለ ትምህርት ጥራት ልብን የሚያሞቅ ሪፖርት ዘርዝረዋል። ታዲያ ይህንን “የምስራች” የሚያፈርስ “የመበየጃ” ዜና ወዲያውኑ ተከትሎ መቅረቡ አይገርምም?

“ከዳያስፖራ ደጋፊዎች የምናገኘው ምላሽ አበረታች ነው”

በአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የውጭ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢና በመድረክ የብሔራዊ ምክር ቤት አባል የሆኑት አቶ ተመስገን ዘውዴ፤ በሁለቱ ድርጅቶች ወቅታዊ ጉዳይ ላይ ለመምከርና በዲፕሎማሲና በፋይናንስ ድጋፍ ዙሪያ ከውጭ ደጋፊዎቻቸው ጋር ለመወያየት ትላንትና ወደ አሜሪካ ተጓዙ፡፡ በአንድነት እቅድና ስትራቴጂ መሠረት የውጭ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴው በጊዜው ከኢትዮጵያ ውጭ ያሉ ኢትዮጵያዊያን ደጋፊዎች በዲፕሎማሲ እና በፋይናንስ ፓርቲውን የሚረዱበትን ሁኔታ ማፈላለግና በሀገራቸው ጉዳይ እንዲደራጁ የማድረግ ሃላፊነት እንዳለበት የገለፁት አቶ ተመስገን፤ ጥረቱ በፊት የተጀመረ እንደሆነና ይህንኑ ጥረት አጠናክሮ ለመቀጠል ወደ አሜሪካ መጓዛቸውን ተናግረዋል፡፡

“ከዚህ በፊት እንደተለመደው በሀገሪቱ ወቅታዊ ጉዳይ፣ ስለ አደረጃጀትና የፋይናንስ ድጋፍ ለደጋፊዎች ገለፃ አደርጋለሁ” ያሉት አቶ ተመስገን፤ ጉዟቸው ዋሽንግተን ዲሲ፣ ካናዳና ደቡብ አፍሪካን እንደሚሸፍን ገልፀዋል፡፡ ቀደም ባለው ጊዜ በአሜሪካ 10 ያህል ግዛቶች ተዘዋውረው አባላትን አደራጅተው መመለሳቸውን ገልፀው፤ በአሁኑ ጉዞ በአሜሪካ ውስጥ የሚዘዋወሩባቸው ስቴቶች አሜሪካ በሚገኙ የድርጅት ሃላፊዎች ፕሮግራም እንደሚወሰን ተናግረዋል፡፡ ድጋፍ በማሰባሰብ፣ በአደረጃጀት፣ በዲፕሎማሲና በፋይናንስ ድጋፍ ለሚሠሩት ሥራ አምስት ወራትን በአሜሪካ በካናዳና ደቡብ አፍሪካ እንደሚቆዩና ነሐሴ መጨረሻ አሊያም መስከረም መጀመሪያ ላይ ወደ ሀገራቸው እንደሚመለሱ አቶ ተመስገን ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

የአንድነትና የመድረክ ደጋፊዎች በተለይ በዋሽንግተን ዲሲ ሲያትል፣ በካሊፎርኒያ ቦስተን፣ አትላንታ፣ በዴንቨርና በሌሎች በርካታ ግዛቶች እንደሚገኙ ገልፀው የድርጅቱ ሃላፊዎች ባላቸው ፕሮግራም ቢቻል ሁሉንም አዳርሰው፣ አደረጃጀቱንና የፋይናንስ ድጋፉን ለማጠናከር እንደሚጥሩ ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ የተቃውሞ ፖለቲካ በመቀዛቀዙ የዲያስፖራውም ድጋፍ ተቀዛቅዟል በሚባልበት በአሁኑ ወቅት ከውጭው ደጋፊ ምን ይጠብቃሉ ተብለው ለተጠየቁት ሲመልሱ “ኢትዮጵያዊያን ደጋፊዎቻችንና ወገኖቻችን በምንም ሁኔታ ውስጥ ሆነው ስለገራቸው ያላቸው ስሜት ከፍተኛ ነው” ያሉት አቶ ተመስገን፤ አንድነትም ሲያደራጃቸው በህጋዊና በሠላማዊ መንገድ በመሆኑ ህጋዊ የዴሞክራሲ ሽግግር እንዲኖር የሚፈልጉ ኢትዮጵያዊያን በምንም ሁኔታ ከመደራጀትና ከመደገፍ ወደኋላ እንዳላሉ፣ ተቀዛቅዟል የሚባለውም ሀሰት እንደሆነ ተናግረዋል።

“እነዚህ በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ህጋዊ የስልጣንና የዴሞክራሲ ሽግግር እንዲኖር ፍላጐት ያላቸው ስለመሆኑ በደንብ እናውቃለን” ብለዋል። የሀገራቸው የልማትና የደህንነት ጉዳይ፣ የሰብአዊ መብት መከበር፣ የህዝብ የስልጣን ባለቤትነት የሚያገባቸው በመሆኑ የሀገር ውስጥ ሠላማዊ ትግልን ከመደገፍ፣ ከመደራጀትና በሠላማዊ መንገድ ከመታገል ቦዝነው እንደማያውቁ በአጽንኦት የገለፁት ሃላፊው፤ በአንድነትና በመድረክ ደጋፊዎች መካከል አንዳችም መቀዛቀዝ እንዳልታየ ተናግረዋል፡፡

“ይህን ጉዳይ ከዚህ ቀደም ወደ እነርሱ እየሄድን ስናደራጅና ስንቀሰቅስ አይተነዋል” ያሉት አቶ ተመስገን፤ ዛሬም እንደተለመደው ሠላማዊና ህጋዊ ትግሉን አጠናክሮ በመቀጠል የኢትዮጵያ ህዝብ የስልጣን ባለቤት እንዲሆን፣ ሰብአዊ መብቱ እንዲጠበቅ፣ የመድብለ ፓርቲ ስርዓትና ዴሞክራሲ በዚህች አገር እውን እንዲሆን መታገል እንዳለባቸው እንደሚያስረዱ ገልፀዋል፡፡ በዚህም እንደ በፊቱ ሁሉ ስኬታማና የተዋጣለት የማደራጀትና የድጋፍ ማሰባሰብ ስራ ሰርተው እንደሚመለሱ እምነታቸውን ገልፀዋል፡፡ “እንኳን እዚያ ሄደን አገር ውስጥም ሆነን ከዳያስፖራ ደጋፊዎች የምናገኘው ምላሽ አበረታች ነው” ብለዋል - አቶ ተመስገን፡፡

ውስብስብነቱ ለማተሚያ ቤት አስቸጋሪ ሆኗል

ህገወጥ የመቶ ዶላር ኮፒዎችን ለመከላከል፣ በአዲስ ዲዛይን የተሰራ ባለ 100 ዶላር ኖት ከስድስት ወር በኋላ ስራ ላይ እንደሚውል የአሜሪካ ብሄራዊ ባንክ (ፌደራል ሪዘርቭ) ባለፈው ረቡዕ ገለፀ። የተጠማዘዘ ሰማያዊ ጥለትና ሌሎች አስቸጋሪ ገፅታዎች ተጨምረውበት የተሰራው ዶላር፣ ከሁለት አመት በፊት ጥቅም ላይ እንዲውል ታስቦ የነበረ ቢሆንም፣ ህትመት ላይ በተፈጠረ ችግር ሲጓተት ቆይቷል። አስመስሎ መስራትን ለመከላከል ተብለው የተጨመሩ ዲዛይኖች ናቸው ህትመት ላይ የመጨማደድ ብልሽት እየፈጠሩ ያስቸገሩት።

በተለይ በዶላሩ ውስጥ የተጠቀቀለለ የሚመዝል ስስ ሪባን ለህትመት በጣም ፈታኝ በመሆኑ፣ የማተሚያ ማሽኖች ላይ ማስተካከያ ማድረግ አስፈልጓል። ሪባኑ ከጥቃቅን ሌንሶች የተሰራ ሲሆን፣ ዶላሩን ወደቀኝ ገፋ ሲደረግ ሪባኑ ወደ ግራ የሚንሸራተት ሆኖ ይታያል ብለዋል የማተሚያ ቢሮ ቃል አቀባይ ዳውን ሃሌ። ዶላሩን ቀና ደፋ በማድረግ፣ ሪባኑ ላይ የሚታዩት የደወል ምስሎች፣ “100” ወደሚል ፅሁፍ ይቀየራሉ። የቀለም ብልቃጥ ምስል ላይ የተጨመረው የደወል ምስል ደግሞ፣ መልኩ ከብጫ ወደ አረንጓዴ ይለወጣል።

በትልቁ የተጻፈው “100” የሚል ቁጥርም እንዲሁ ቀለሙ ይቀያየራል። ነባሩ ዲዛይን ለተወሰኑ አመታት አገልግሎት ላይ እንደሚቆይ የገለፀው የአሜሪካ ቢሄራዊ ባንክ፣ በዚህ አመት 250 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ባለመቶ ዶላር ኖት በአዲሱ ዲዛይን እንደሚታተም አስታውቋል (2.5 ቢሊዮን ኖቶች መሆኑ ነው)። የማሻሻያ ዲዛይኑ የተጀመረው ከአስር አመት በፊት ሲሆን፣ በመጀመሪያ ባለ 20 ዶላር ላይ የቀለማት ለውጥ ከተደረገለት በኋላ፣ ባለ 50፣ ባለ 10 እና ባለ 5 ዶላር ኖቶችም ተሻሽለው ወጥተዋል። የአንድ ዶላር ኖት፣ ምንም ለውጥ አልተደረገበትም።

Saturday, 27 April 2013 10:21

የቢሊዮነሮች መንደር

ለእረፍት ጊዜና ለመዝናኛ የሚፈለጉ አሸዋማ የባህር ዳርቻዎች በጣም ውድ ናቸው። ካርበን የተሰኘችው የካሊፎርኒያ መንደር ደግሞ የአለማችን እጅግ ውድ የባህር ዳርቻ ነች። በእረፍት ጊዜ ጎራ የሚሉበትን ቤት በመግዛት ወይም በመገንባት፣ በካርበን የባህር ዳርቻ፣ ከጫፍ እስከ ጫፍ የተደረደሩት ቢሊዮነሮችና ሚሊዮነሮች ናቸው - ፎርብስ መፅሄት እንደዘገበው። 1. (ጆል ሲልቨር)፡ “ማትሪክስ” በተሰኙት ፊልሞች ከፍተኛ ገቢ ያገኘው ሲልቨር፣ በአካባቢው ከ80 አመት በላይ ያስቆጠረ የተንጣለለ ቤት በ$14.4 ሚሊዮን ገዝቷል። ሁለት ቢሮ፣ ጂም፣ መዋኛና የቴኒስ መጫወቻ አሉት። 2. (ፖል አለን)፡ ከቢል ጌትስ ጋር ማይክሮሶፍትን በመመስረት ዛሬ የ$15 ቢሊዮን ጌታ የሆነው ፖል አለን፣ አምስት መኝታ ቤት፣ ፊልም መመልከቻ ክፍል እንዲሁም መዋኛ ያካተተውን ዘመናዊ ቤት በ$25 ሚሊዮን ገዝቷል። 3. (ጄሚ ማካርት)፡ ሚሊዮነሯ በዚህ የባህር ዳርቻ ከአንዲት የፊልም ተዋናይት የገዛችው ቤት ከ$27 ሚሊዮን በላይ የሚያወጣ ነው። 4. (አሮን ሚልካን)፡ በፊልም ኩባንያ ሃብት ያፈራው አሮን ሚልካን የ$4.2 ቢሊዮን ጌታ ነው።

ከ15 አመት በፊት የገዛው ቤተመንግስት የመሰለ 6 መኝታ ቤት፣ የተንጣለለ መዋኛና የፊልም ማሳያ ክፍል አሉት። ዋጋው $7.3 ሚሊዮን ነው። 5. (ሄም ሳባን)፡ የቴሌቪዥን ቢዝነስን ጨምሮ በበርካታ ኢንቨስትመንቶች የ$3.1 ቢሊዮን ባለቤት የሆነው ሳባን፣ $8.1 ሚሊዮን የሚያወጣው የእረፍት ጊዜ መኖሪያ ቤቱ፣ 9 መኝታ ቤቶችን ይዟል። 6. (ጀፍሪ ካትዘንበርግ)፡ በፊልም ኩባንያ ድሪምወርክስ ውስጥ ከፍተኛ ድርሻ ያለው ካትዘንበርግ፤ ባለ መዋኛ መኖሪያ ቤቱ $3.3 ሚሊዮን ያወጣል። 7. (ላሪ አሊሰን)፡ የኦራክል ኩባንያ መስራች በአለማችን 5ኛው ሃብታም አሜሪካዊ ነው። ሃብቱ $43 ቢ ይገመታል። አምና 9 መኝታ ቤቶች ያሉት ባለ3 ፎቅ መኖሪያ ቤት የገዛው በ$37 ሚሊዮን ነው። በአካባቢው ከ10 በላይ ቤቶችን ገዝቷል። 8. በሬስቶራንት ስራ ሚሊዮነር የሆነው ፒተር ሞርተን ከ15 አመት በፊት በገዛው መሬት $3.4 ሚሊዮን የሚያወጣ የተንጣለለ ቤት አለው።

9. ከሆሊውድ የመዝናኛ ንግድ ወደ ሬስቶራንት ቢዝነስ የገባው ሜር ቲፐር፣ አምስት መታጠቢያ ገንዳዎችን የያዘ ባለሁለት መኝታ ቤት ንብረቱን የገዛው ከ20 አመት ገደማ በፊት ነው። ዋጋው $2 ሚሊዮን 10. ከቢሊዮነሮች ተርታ የተሰለፈው ካናዳዊ ጀራልድ ሽዋርትዝ፣ ከአምስት አመት በፊት ሶስት ጎረቤታም ግቢዎችን ገዝቶ ያስገነባው ግዙፍ ቤት $19 ሚሊዮን ያወጣል። ጠቅላላ ሃብቱ $1.4 ቢሊዮን ነው። 11. በሙዚቃና በፊልም ቢዝነሶቹ ከአለማችን ሁለት መቶ ሃብታሞች መካከል አንዱ የሆነው ዳቪድ ጋፈን፣ 4 ግቢዎችን ገዝቶ በማዋሃድ ነው መዋኛ ገንዳ ያለው ቤት የገነባው። ዋጋው $6 ሚሊዮን ነው። ጠቅላላ ሃብቱ ደግሞ $6 ቢሊዮን። 12. ኢሊ ብሮድ ከ14 አመት በፊት በገዛቸው ሁለት ግቢዎች ላይ ያሰራው፣ መስተዋት የበዛበት ቤት $5.1 ሚሊዮን ያወጣል። በአሜሪካ ባሉት የተለያዩ ኢንቨስትመንቶች $6.3 ቢሊዮን ባለሃብት ሆኗል።