Administrator

Administrator

ከአንድ ጋዜጣ ያገኘነው ተረት የሚከተለውን ይመስላል፡- ተረቱ በተለያየ አገር የሚነገር ቢሆንም በዚህ መልኩ የተነገረው እኛ ጋ ነው፡፡ እንደሚያመች አድርገን አቅርበነዋል፡፡
 እነሆ፡-
ከዕለታት አንድ ቀን ጅብና ቀበሮ ቤት ፍለጋ ይሄዳሉ፡፡ ጅብ ትልቅ ቤት ሲያገኝ፣ ቀበሮዋ ብዙ ቀዳዳዎች ያሉት ትንሽ ቤት አገኘች፡፡ ቀበሮዋም፤
“አንበሳ ቢመጣብህ በየት በኩል ታመልጣለህ? እኔ በቀዳዳዎቹ ለማምለጥ እችላለሁ” ትለዋለች ለጅቡ፡፡
ጅብ ብዙም አርቆ ሳያስተውል፣
“እባክሽ እንቀያየር?” ይላታል፡፡
እሺ፤ብላው ተቀያየሩ፡፡
ሌላ ቀን ጅቡና ቀበሮዋ ምግብ እንፈልግ ተባባሉ፡፡
ጅብ፤
 “ወፍራም በሬ አግኝቻለሁ፤ አንቺስ?” አላት፡፡
ቀበሮ ያገኘችው ተባይ የሞላው አህያ ነው፡፡
“እኔ ያገኘሁት አህያ ነው፡፡ ግን ተመልከት ጮማ ነች! እንቀያር” አለችው፡፡
ተቀያየሩ፡፡
የማረጃ ቢላዋ ፍለጋ ተሰማሩ፡፡
ጅብ ቢላ አገኘ፡፡ ቀበሮ ዶሮ ላባ አገኘች፡፡
“ዶሮ ላባ በጣም ጠቃሚ መሳሪያ ነው፡፡ ቢጠፋብኝ በቀላሉ እተካዋለሁ፡፡ ያንተ ቢላ ግን ቢሰበር መተኪያ የለህም፤እንቀያየር” አለችው፡፡
ጅብ ተስማማ፡፡ ተቀያየሩ፡፡
በሬውን ለማረድ ጅቡ አልቻለም፡፡ ቀበሮ ግን ቢላውን በላባ ሸፍና በሬውን አረደችና አብረው በሉ፡፡ ቆይተው በመንገድ ላይ ማርና ቅቤ የተሸከመ ግመል አዩ፡፡ ቀበሮ፣ ግመሉን ለሚነዱት ሐማሎች፤
“ደክሞኛል፤ እባካችሁ ግመሉ ላይ ጫኑኝ” አለች፡፡ ጫኗት፡፡
ማሩንና ቅቤውን ግጥም አድርጋ በላች፡፡
 “አውርዱኝ ቤቴ ደርሻለሁ” አለች፤ጥግብ ስትል፡፡ አወረዷትና ወደ ገበያ ሄዱ፡፡ እዚያ ሲደርሱ “ጉድ!” አሉ። የተሰሩት ገባቸው፡፡ በቁጭትና በንዴት የአካባቢውን ቀበሮዎች ሁሉ ሰበሰቡና፤ “ዝለሉ!” አሉ፡፡ ያቺ ቀበሮ ቅቤና ማሩ ስለሚከብዳት እንደ ልቧ ስለማትዘል በቀላሉ ሊለይዋት ነው! እውነትም እመት ቀበሮ መዝለል አቅቷት ተያዘች። ታሰረች፡፡ “በኋላ እንገርፋታለን” ብለው ወደ ገበያው ሄዱ፡፡
 ያ ጅብ መጣና አገኛት፤  
“ለምንድነው የታሰርሺው?” ሲል ጠየቃት፡፡
“ቅቤና ማር ብይ ሲሉኝ እምቢ ብዬ!” አለችው፡፡
ጅቡም፤ ብልጥ የሆነ መስሎት፤
“በይ ቦታ እንለዋወጥ!” አላት፡፡ ፈታትና ቦታ ተለዋወጡ፡፡
ነጋዴዎቹ ሲመለሱ፣ በቀበሮዋ ቦታ ጅቡን አገኙ፡፡
“ምን ልትሰራ መጣህ?” አሉት፡፡
“ቀበሮ ቅቤና ማር ታገኛለህ ብላኝ ነው!” አላቸው፡፡
ቀበሮ ዛፍ ላይ ሆና፣
“ዐይኑን አትግረፉት! ጆሮውን አትንኩት! ሌላ ቦታ ላይ ግን ግረፉት” ትላለች፡፡
ሰዎቹ እንዳይሞት እንዳይድን አድርገው ገረፉት፡፡ ቆዳው ተልጦ ሥጋው ይታይ ጀመር፡፡ ከዚያ ጥለውት ሄዱ፡፡
ጅቡ ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ ቤት ሲደርስ ልጆቹ ሲያዩት፤
“አባታችን ስጋ ይዞልን መጣ” ብለው ራሱን ተቀራመቱት!
*       *     *
ከላይኛው ተረት የቤትን ችግር ማስተዋል አያዳግተንም፡፡ ነገ ጠላት ቢያጋጥም ለማምለጥ ማስተዋል እንዳለብን ልብ እንላለን፡፡ ቦታ በመቀያየር ዙሪያ ብዙ ጅልነት እንደሚኖር እናጤናለን፡፡ ምግባችንን መለዋወጥም የራሱ ጣጣ እንዳለው እንገነዘባለን፡፡ ማረጃችን ቢላ ወይስ ዶሮ - ላባ? የሚለውንም እናሰምርበታለን፡፡ ቢላ በላባ ሸፍነው ማረድ ግን ማኬቬሊያዊ አካሄድ ነው! የማርና ቅቤ ተሸካሚ ግመል፣ ግመሉንም የሚነዱ ነጋዴዎች ብዙ ናቸው፡፡ ግመሉ ላይ የሚጫኑ ብልጣ - ብልጦች ግን አያሌ ናቸው፡፡ ያም ሳይበቃቸው እንደ ጅቡ ሁሉ ለብዙዎች መታሰር ምክንያት የሚሆኑ አያሌ ናቸው! በልተው፣ መብላታቸው ተነቅቶባቸውም በአፋቸው ሌሎችን አስቀፍድደው፤ ዛፍ ጫፍ ላይ ሆነው የሚያላግጡ በርካቶች ናቸው! ለማን አቤት ይባላል?! ጅልነት በራስ ወገን እስከ መበላት ያደርሳል! “አብዮት ልጇን ትበላለች!” ይሉ ነበር የዱሮ ገዢዎቻችን፡፡
ሎሬት ፀጋዬ እንዳለው፤
“አንዲት የዱር አውሬ፣ በአንዳንድ የመከራዋ ሰሞን
ልጇን ትበላለች አሉ፣ ምጥ የጠናባት እንደሆን!
ዕውነቱ ሁሌም አይቀሬ ነው፡፡ ዩኒቨርሳል እንደሆነው ሁሉ “የቤት - ጣጣም” አለበት፡፡ ዲበ - ኩሉ ይሰውረን እንጂ በሹም - ሽር የምንገላገለውስ አይደለም! “ጉልቻ ቢቀያየር ወጥ አያጣፍጥም” የሚለው ተረት ዱሮ ይሰራ ነበር፡፡  
አሁን ግን፤
‹‹የጣፈጠ ወጥ በጉልቻ መቀያየር የሚበላሽበት ዘመን መጣ›› በሚለው መተካት ሳያሻው አይቀርም፡፡ ሁሉን ነገር በሙከራ ብቻ አንዘልቀውም፡፡ ከወገናዊነት ነፃ እንሁን፡፡ ከልባችን ወደፊት እንጓዝ!!
አገሪቱ ከቤተ ሙከራነት መውጣት አለባት፡፡ በመካከለኛው የቢሮክራሲ ማዕድ የሚነሳውን ቢሮክራሲያዊ ሙስና አባዜ መላቀቅ ያሻል! ግምገማ ዕውነተኛ መሆኑ መፈተሽ አለበት፡፡ ባጠፉ አመራሮች ላይ እርምጃ እንወስዳለን ሲባል፣ ሁለት ነገሮች ግንዛቤ ውስጥ መግባት አለባቸው፡፡ አንደኛው ገምጋሚዎቹ ምን ያህል ንፁሀን ናቸው? ሁለተኛ የሚወሰደው እርምጃ ምን ያህል ሥር ነቀል ነው? ለእነዚህ ጥያቄዎች አዎንታዊ ምላሽ ማግኘት ወሳኝ መሆኑን አንዘንጋ! ከዚህ ሁሉ በኋላ ደግሞ በቦታቸው የሚተካውስ ማነው? አስተማማኝ ነውን? ብሎ መጠየቅም ያባት ነው! ዞሮ ዞሮ ከሥርዓቱ መመሪያ ውጪ አዲስ ነገር የለም! ጆርጅ ፍሪድማን፤ ‹‹ቀጣዮቹ መቶ ዓመታት›› (The next 100 years ) በሚለው መጽሐፉ፤
‹‹ኦባማ የቡሽን የውጪ ጉዳይ ፖሊሲ አራማጅ ነው፡፡ ቡሽ በኢራቅ ላይ ያወጣው መመሪያ እንዳለ አለ። ከአውሮፓውያን በተለይም ከጀርመን ያለው ግንኙነት ያው ነው፡፡ ከኢራንና ከኩባ ጋር ለመግባባት የሞከረው ውጤቱ ፍሬ ቢስ ነበር፡፡ ከሩሲያ ጋር ያለውም ዝምድና የቡሽ እንደነበረው ነው፡፡ ከጆርጂያ፣ ከዩክሬን.. ከፖላንድም ያለውን ዝምድና ማዝለቅ ነው፡፡ ኦባማ ለፕሬዚዳንትነት በመወዳደርና ፕሬዚዳንት በመሆን መካከል ያለውን ልዩነት ጥርት አድርጎ ያውቃል፡፡ እንደ ተመራጭ ብዙ ነገር ትናገራለህ፡፡ እንደ መሪ ግን ከነባራዊው ዕውነታ ጋር ትጋፈጣለህ። እንደ ቼዝ ተጫዋች የምትሄድበት አቅጣጫ ይጠፋሃል፡፡ መሪነት የዋዛ ነገር አይደለም፡፡”
ዶናልድ ትራምፕም ከመመሪያው ውጪ እንዳይደለ ከላይ ካነሳነው ሁኔታ መገንዘብ አያዳግተንም፡፡ የሀገራችንን አመራሮችም ሆነ የመካከለኛ ቢሮክራሲ ሹማምንት በዚህ ረገድ መገምገም አዳጋች አይደለም፡፡
እንደ ፀሀፊው አሪፍ አገላለፅ፤
‹‹United States is a bizarre mixture of overconfidence and insecurity›› (አሜሪካ ከመጠን ያለፈ ልበሙሉነትና ደህነነቷን የማጣት ሥጋት ቅልቅል የሆነች አገር ናት እንደ ማለት ነው) ይላታል፡፡ እኛስ ብንሆን? ብሎ መጠየቅ አስማታዊነትን አይጠይቅም፡፡ የትኛውም መሪ፣ መካከለኛ መሪ፤ ወይም ታህታይ መሪ፤ በፓይለቶች ቋንቋ፡-
‹‹Soft-Landing›› በሰላም መሬት መድረስ ካጋጠመው ዕድለኛ ወይም የበቃ ሰው ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ አያጋጥምም፡፡ እጅግ ወደ ፅርሃ-አርያም ለወጣ ምድር ሩቅ ናት፡፡ ስለዚህ አዕምሮውን ማዘጋጀት አለበት - ለመውረድ። አለበለዚያ ዐረቦች፤
‹‹ንጉሥ ሆኖ ሳይከሳ የሚሰናበት የለም!” የሚሉትን ተረትና ምሣሌ ልብ እንድንል እንገደዳለን!

Saturday, 12 November 2016 13:49

ከትራምፕ ድል ማግስት...

 - በቅስቀሳቸው ወቅት አደርገዋለሁ ያሉትን ሁሉ ያደርጉት ይሆን?...
         - ከነጩ ቤት ወደ በፊት ፍርድ ቤት ያመራሉ
         - አይሲስ እና አልቃይዳ በትራምፕ ድል ፈንድቀዋል
      በስተመጨረሻም...
አወዛጋቢው ሰውዬ ሰተት ብለው ወደ ነጩ ቤት መግባታቸውን አረጋገጡ፡፡
ዓለም የሰማችውን ለማመን ተቸገረች። ባልተጠበቀ መንገድ የተቋጨው የዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ፣ የአለማችን መነጋገሪያ ትኩስ ትንግርት ሆነ፡፡
የምርጫ ውጤቱ ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ የተለያዩ አለማቀፍ መገናኛ ብዙሃን ካወጧቸው ዘገባዎች የተወሰኑትን ጨለፍ አድርገን እንመልከት።
እንኳን ደስ አለዎት!...
የትራምፕ አሸናፊነት ከተሰማ በኋላ ፣ ፈጥነው የእንኳን ደስ አለዎት መልዕክት ከላኩት የዓለማችን መሪዎች አንዱ፣ “የትራምፕ ደጋፊ ነው” እየተባሉ በዲሞክራቶች ሲብጠለጠሉ የከረሙት የሩስያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ናቸው፡፡ ፑቲን ከክሪምሊን ባስተላለፉት መልዕክት፤ ተኳርፈው የነበሩት ሩስያና አሜሪካ የሚታረቁበት ጊዜ እንደመጣ ተስፋ አለኝ ብለዋል፡፡ ቻይናም በበኩሏ፣ በምርጫ ቅስቀሳቸው በክፉ ሲያነሱ ሲጥሏት የከረሙትን ትራምፕን “ስለተመረጡ ደስ ብሎኛል፤ የሁለትዮሽ ግንኙነታችንን ለማሳደግ ከአዲሱ የአሜሪካ መንግስት ጋር ለመስራት ፍቃደኛ ነኝ” ብላለች፤ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ በኩል፡፡
የእንግሊዟ ቴሬሳ ሜይ፣ የአፍጋኒስታኑ አሽረፍ ጋና፣ የግብጹ አብዱል ፈታህ አል ሲሲ፣ የህንዱ ናሬንድራ ሞዲ፣ የኬንያው ኡሁሩ ኬንያታ፣ የደቡብ አፍሪካው ጃኮብ ዙማ እና የፍልስጤሙ መሃሙድ አባስ ለትራምፕ የእንኳን ደስ አለዎት መልዕክታቸውን ካስተላለፉ በርካታ የዓለም አገራት መሪዎች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡
የአውሮፓ ህብረት ከፍተኛ ባለስልጣናት በበኩላቸው ለትራምፕ በጻፉት ደብዳቤ፣ የእንኳን ደስ አለዎት መልዕክታቸውን ገልጸው፣ “በቻሉት ፍጥነት ሁሉ ዛሬ ነገ ሳይሉ ወደ አውሮፓ ይምጡና አስቸኳይ ስብሰባ እናድርግ” ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
ያሉትን ሁሉ ያደርጉታል?...
አወዛጋቢው ዶናልድ ትራምፕ በምርጫው አሸንፈው መንበረ ስልጣኑን መረከባቸው፣ በአሜሪካና በተቀረው አለም ላይ ምን አይነት ለውጥ ያመጣ ይሆን? የሚለው ጥያቄ ብዙዎችን እያነጋገረ ያለ ጉዳይ ነው፡፡ ሰውዬው ስልጣን ብይዝ አደርጋቸዋለሁ በሚል በምርጫ ቅስቀሳቸው ወቅት የተናገሯቸውን አስገራሚና አስደንጋጭ ጉዳዮች፣ በእርግጥ ስልጣን ላይ ሲወጡ ይተገብሯቸው ይሆን? ከተገበሯቸውስ ምን አይነት ለውጥ ይመጣ ይሆን? ብለው በጉጉት የሚጠይቁ በርክተዋል፡፡
ብዙዎች ይህን ጥያቄ ለመመለስ የየራሳቸውን አስተያየት እየሰጡ ሲሆን ቢቢሲም የትራምፕ ፕሬዝደንት መሆን አገሪቱ ከተቀረው አለም ጋር ባላት ግንኙነት ላይ ይፈጥራቸዋል ያላቸውን ቁልፍ ለውጦች ዘርዝሯል፡፡
ትራምፕ በያዙት የንግድ ፖሊሲ የሚገፉበት ከሆነ፣ አሜሪካ ከተቀረው አለም ጋር ባላት የንግድ ግንኙነት ላይ ከፍተኛ ለውጥ መምጣቱ አይቀሬ ነው ይላል ቢቢሲ፡፡ ለስራ አጥነት ምክንያት ሆነዋል ያሏቸውንና አገሪቱ ከሌሎች አገራት ጋር የገባቻቸውን ነባር የነጻ የንግድ ስምምነቶች ሊያፈርሱ፤ ከአለም የንግድ ድርጅት አባልነቷ እንድትወጣ አደርጋለሁ ያሉትን እቅዳቸውንም ተግባራዊ ካደረጉ እጅግ ትልቅ ለውጥ ይፈጠራል ይላል፡፡
አሜሪካ አምና ከ195 የአለማችን አገራት ጋር የተፈራረመቺውን የፓሪሱ የአየር ንብረት ለውጥ ስምምነት እንደሚያፈርሱና ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሙቀት መጠን መጨመር ፕሮግራሞች የምትሰጠውን ገንዘብ እንደሚያቋርጡ መናገራቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ እንዳሉት የሚያደርጉ ከሆነ ሌላ ለውጥ ሊታይ ይችላል ብሏል።
አገሪቱን ከሜክሲኮ የሚያካልል የግንብ አጥር የመገንባት፣ ከኔቶ ጋር ያለመቀጠልና ከሩስያ ጋር የነበረውን የተካረረ ግንኙነት የማለዘብ እቅዶቻቸውም፣ የመተግበር ዕጣቸው እውን ከሆነ ተጽዕኗቸው እጅግ የጎላ ይሆናል ይላል፤ ቢቢሲ። ኒውዮርክ ፖስት ግን፣ ትራምፕ በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ቃል የገቧቸውን ጉዳዮች በእርግጥም ስልጣን ላይ ሲወጡ ተግባራዊ ስለማድረጋቸው ይጠራጠራል፡፡ ዘገባው እንደሚለው፤ ትራምፕ በተለይ ዋና ዋናዎቹን ቃል የገቧቸው ጉዳዮች ተግባራዊ ለማድረግ፣ የኮንግረሱን ድጋፍና ይሁንታ ማግኘት ግድ ይላቸዋል፡፡ እርግጥ ሪፐብሊካኖች በሁለቱም ምክር ቤቶች አብላጫ ድምጽ ያላቸው መሆኑ፣ ጉዳዩን ያን ያህል ፈታኝ ላያደርገው ይችላል።
ይሄም ሆኖ ግን፣ ትራምፕ የተወሰኑ ለውጦችን የማድረግ ስልጣንና አቅም ባያጡም፣ በምርጫ ቅስቀሳቸው ወቅት ቃል የገቡትን የወፈፌ ሃሳብ የሚመስል ዕቅድ ሁሉ፣ መንበረ ስልጣኑን ስለተቆናጠጡና የእሳቸው ሃሳብ ስለሆነ ብቻ ያለ ከልካይ ተግባራዊ ያደርጉታል ብላችሁ አትስጉ ያለው ደግሞ ዋሽንግተን ፖስት ነው፡፡
እዚያም ምርጫን ተከትሎ አመጽ...
አሁን...
የምርጫ ውጤት ይፋ መደረግን ተከትሎ የሚመጣ አመጽና ተቃውሞ የእነ አፍሪካ መገለጫ ብቻ አይደለም! ልዕለ ሃያል አሜሪካም፣ የምርጫ ውጤትን በጸጋ ከመቀበል ወደ አመጽና ተቃውሞ ወርዳለች፡፡ ትራምፕ ማሸነፋቸው ከታወቀ በኋላ በካሊፎርኒያ በመቶዎች የሚቆጠሩ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች አደባባይ ወጥተው ተቃውሟቸውን ማሰማታቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡ በምርጫው ውጤት ያልተደሰቱት ከ500 በላይ የሚሆኑ ተማሪዎች ረቡዕ ማለዳ አደባባይ በመውጣት ጸረ- ትራምፕ መፈክሮችን ማሰማታቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ በበርክሌይ፣ ኤርቪንና ሳንጆሴ አካባቢዎችም ተመሳሳይ አነስ ያሉ ተቃውሞዎች መደረጋቸውን ገልጧል፡፡ የትራምፕን አሸናፊነት አምነው ለመቀበል ያልፈለጉ በሺህዎች የሚቆጠሩ አሜሪካውያን፣ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች አደባባይ ወጥተው ተቃውሟቸውን ማሰማታቸውን ቀጥለዋል፡፡ በርካታ አሜሪካውያን ማንሃታን ውስጥ ወደሚገኘው ግዙፉ የትራምፕ ህንጻ በማምራት ሰውዬው በስደተኞችና በሙስሊሞች ላይ የያዙትን አቋም በመንቀፍ፣ ለመሪነት አይበቁም ሲሉ ተቃውመዋል፡፡ በኦክላንድም 6 ሺህ ያህል የትራምፕ ተቃዋሚዎች አደባባይ ወጥተው የትራምፕን ፎቶግራፍ አቃጥለዋል፣  የመደብሮችን መስኮቶች ሰባብረዋል፡፡ ወደ ትራምፕ ኢንተርናሽናል ሆቴል ሲያመሩ የነበሩ 1 ሺህ 800 ተቃዋሚዎችም በፖሊስ እገዳ ተመልሰዋል፡፡
ትራምፕ ፕሬዝዳንታችን አይደለም የሚል መፈክር ያነገበው ተቃውሞው፤ ወደ ሎሳንጀለስ፣ ፖርትላንድ፣ ዋሽንግተን ዲሲ፣ ፊላዴልፊያ፣ ቦስተን፣ ሲያትል፣ ሳን ፍራንሲስኮና ሌሎች የአሜሪካ አካባቢዎች መዛመቱን ቢቢሲ የዘገበ ሲሆን፣ ዘረኝነትን የሚያወግዙ 200 ያህል እንግሊዛውያንም ለንደን በሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ደጃፍ ባደረጉት ተቃውሞ ትራምፕን አውግዘዋል ብሏል - ዘ ኢንዲፔደንት፡፡
አይሲስና አልቃይዳ በደስታ ፈንጥዘዋል
“ላሸንፍ እንጂ ሙስሊሞች የአገሬን ምድር አይረግጡም!...” የሚለው የትራምፕ ንግግር ብዙዎችን አስደንግጦ ነበር፡፡ ይህ ንግግር ብዙዎችን ቢያስደነግጥና ቢያስከፋም፣ አይሲስን ለመሳሰሉ ጽንፈኛ ቡድኖች የተለየ ትርጉም ነበረው። የሰውዬው ንግግር በሙስሊሞች ላይ ቁጣን የሚቀሰቅስ ከመሆኑ በተጨማሪ፣ ለእነዚህ ቡድኖች አዳዲስ አባላትን መመልመያ ፕሮፓንዳ ሆኖላቸው ነበር። የአይሲስ እና የአልቃይዳ አጋሮች የሆኑ አክራሪ ቡድኖች ባለፈው ረቡዕ የዶናልድ ትራምፕን ማሸነፍ ሲሰሙ፣ እንደ አንድ የሪፐብሊካን ደጋፊ በደስታ ነበር የፈነጠዙት፡፡
ዋሽንግተን ፖስት እንደ ዘገበው፤ ከአይሲስ ጋር ግንኙነት ያለው አል ሚንባር ጂሃዲ የተባለ ሚዲያ፣ “በፈጣሪ ድጋፍ አሜሪካን በገዛ እጃቸው የሚያጠፏት ሰው በፕሬዚዳንትነት ተመረጡ!... የእሳቸው መመረጥ ሙስሊሙ በአሜሪካ ላይ ጥላቻ እንዲኖረው ያደርጋል” ብሏል፡፡ የአይሲስ ጂሃዲስት ታጣቂዎች፣ “አህያው ትራምፕ መመረጡ የአሜሪካ ውድቀት ምልክት ነውና በማሸነፉ ደስተኛ ነን” ሲሉ መናገራቸውንም ዘ ዴይሊ ሚረር ዘግቧል፡፡
ዘ ሰን በበኩሉ፤ አሸባሪው ቡድን አል ቃይዳም የትራምፕ ማሸነፍ ለአሜሪካ ጥፋት በር የሚከፍት በመሆኑ እንዳስደሰተው መግለጹን በመጠቆም፣ ቡድኑ በምርጫው ሰሞን በአሜሪካ የሽብር ጥቃት ለመፈጸም አቅዶ እንደነበር ደርሼበታለሁ ሲል ኤፍቢአይ አስታውቆ እንደነበርም ዘግቧል፡፡
ሄላሪን በሚሼል?
በርካታ አሜሪካውያን ለሄላሪ ክሊንተን ድምጻቸውን በመስጠት በአገሪቱ ታሪክ የመጀመሪያዋን ሴት ፕሬዚዳንት ወደ ስልጣን ለማምጣት ቋምጠው ነበር ይላል፤ ዘ ዴይሊ ቴሌግራፍ፡፡ ያልተጠበቀው የምርጫ ውጤት ግን፣ ለሄላሪ የታጨውን መንበር ለትራምፕ አሳልፎ በመስጠት ህልማቸውን አጨናገፈው፡፡
በዚህ ዱብ እዳ የተናደዱት ሴት መሪ ናፋቂ አሜሪካውያን፣ ዘንድሮ በሄላሪ ያጡትን ስኬት ከአራት አመታት በኋላ በሚሼል ኦባማ ከእጃቸው ለማስገባት አቅደዋል ተብሏል፡፡አንደበተ ርዕቱዋ ቀዳማዊት እመቤት ሚሼል ኦባማ፣ ከአራት አመታት በኋላ በሚካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ዲሞክራትን ወክለው ቢወዳደሩ ለድል ሊበቁ እንደሚችሉ አስተያየታቸውን የሚሰጡ አሜሪካውያን በርካታ መሆናቸውን ዘገባው ይጠቁማል፡፡
እነዚህ በሄላሪ በለስ ያልቀናቸው ሴት መሪ ናፋቂ አሜሪካውያን፣ ዛሬ ነገ ሳይሉ በትዊተር ድረገጽ ሚሼል2020 የሚል የድጋፍ ዘመቻ መጀመራቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ዘመቻውን የሚቀላቀሉ ዜጎች ቁጥር በአጭር ጊዜ ውስጥ በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉንም አስረድቷል፡፡
የዝነኞች ኩርፊያ
የዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ሂደት፣ ዝነኞች ከወትሮው በተለየ ፖለቲካዊ አቋማቸውን በአደባባይ ያንጸባረቁበት ነበር፡፡ ታላላቅ ድምጻውያን፣ የፊልም ተዋንያን፣ ደራሲያንና የመዝናኛው ኢንዱስትሪ ከዋክብት፣ የሚደግፉትን ዕጩ ተወዳዳሪ ማንነት በይፋ ከመናገር አልፈው፣ አድናቂዎቻቸውም እነሱ ለሚደግፉት ዕጩ ድምጻቸውንእንዲሰጡ በይፋ ቅስቀሳ ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡
ተሸናፊዋ ሄላሪም፣ ወደ ዋይት ሃውስ የሚገቡበትን ጎዳና ይጠርጉልኛል በሚል ቢዮንሴና ጄይዚን ጨምሮ በርካታ ታዋቂ ድምጻውያንን ከጎናቸው አሰልፈው የምረጡኝ ቅስቀሳቸውን ሲያጧጡፉት ከርመው ነበር - አልሆነም እንጂ፡፡
የምርጫ ውጤቱ ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ ምድረ ዝነኛ በድንጋጤ ክው ማለቱን ዘ ቴሌግራፍ ዘግቧል፡፡
“አሜሪካ ሆይ... ተግተሽ ጸልይ!...” ብላለች፤ የሰማችው ነገር ከአቅሟ በላይ የሆነባት ሌዲ ጋጋ፡፡
ከቀናት በፊት ሄላሪን አቅፋ የምርጫ ቅስቀሳ መድረክ ላይ ስትፈካ የታየቺው ድምጻዊት ኬቲ ፔሪ ግን፣ ከጸሎት ይልቅ አብዮት ያዋጣል ባይ ናት። “አብዮት ሊፈነዳ ነው!...” ብላለች፤ ድምጻዊቷ የሄላሪን መሸነፍ ከሰማች በኋላ በትዊተር ገጽ ላይ ባሰፈረቺው ጽሁፍ፡፡“ምንድን ነው እየሆነ ያለው?...” በማለት ግራ መጋባቱን የገለጸው ታዋቂው ራፐር ስኑፕ ዶግ ሲሆን፣ ክሪስ ኢቫንስ በበኩሉ፤ “አሳፋሪ  ነው፤ በጥላቻ የተሞላ ሰው ታላቂቷን አገር ይመራ ዘንድ ፈቅደንለታል!...” በማለት በምርጫው ውጤት መበሳጨቱን ጠቁሟል፡፡
ከትራምፕ ያልተናነሰ የፈነደቀው እንግሊዛዊ
የዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ፣ እጅግ ከፍተኛውን ደስታ ያጎናጸፈው ለአሸናፊው ትራምፕ እንደሆነ አያጠራጥርም፡፡ አንድ እንግሊዛዊ ግን ከትራምፕ ያልተናነሰ በደስታ ፈንድቋል፡፡ ዘ ኢንዲፔንደንት እንደዘገበው፣ ነዋሪነቱ በለንደን የሆነውና ስሙ ያልተጠቀሰው እንግሊዛዊ፣ የምርጫውን ውጤት ከትራምፕ ባልተናነሰ እጅግ በከፍተኛ ጉጉትና ጭንቀት ሲጠባበቅ ነበር፡፡ ሰውዬው የምርጫ ውጤቱን በጉጉትና በጭንቀት የጠበቀው፣ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት በእሱ ህይወት ላይ ያን ያህል ተፅዕኖ የሚፈጥር ስለሆነ አልነበረም፡፡
በምርጫው የሚያሸንፈው ሰው ካሸነፈ በኋላ የሚፈጥረው ነገር ሳይሆን፣ ማሸነፉ በራሱ ነበር እንግሊዛዊውን ያጓጓውም ያስጨነቀውም፡፡ እየጓጓና እየተጨነቀ የምርጫውን ውጤት ሲጠብቅ አመሸ፡፡ በስተመጨረሻም የትራምፕን ድል ሰማና፣ በደስታ ፈነጠዘ፡፡
ትራምፕ ያሸንፋል ብሎ ባስያዘው የቁማር ጨዋታ፣ 200 ሺህ የእንግሊዝ ፓውንድ በላ!
ከነጩ ቤት በፊት፣ ፍርድ ቤት
ሮይተርስ ደግሞ፣ ዘግየት ብሎ አጉል ዘገባ አመጣ...
የታላቂቷ አሜሪካ ቀጣዩ ታላቅ መሪ ዶናልድ ትራምፕ፣ ወደ ነጩ ቤት ከማምራታቸው በፊት ወደ ፍርድ ቤት ማምራታቸው አይቀርም ይላል፤ ሮይተርስ። ዘገባው እንዳለው፣ ዶናልድ ትራምፕ አገልግሎቱን ባቆመው የቀድሞው ትራምፕ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የተመሰረተባቸውን ክስ ለመከታተል፣ ካሊፎርኒያ ውስጥ ወደሚገኝ የፌዴራል ፍርድ ቤት በሳምንታት ጊዜ ውስጥ ያመራሉ፡፡
ምንም እንኳን የአገሪቱ ህግ ፕሬዚዳንቶች ከስራቸው ጋር በተያያዘ ክስ እንዳይመሰረትባቸው ጥበቃ የሚያደርግላቸው ቢሆንም፣ ከስልጣን በፊት በሰሯቸው ጥፋቶች ሊከሰሱ እንደሚችሉ ይደነግጋል ብሏል ዘገባው፡፡
ትራምፕ ከተለያዩ የንግድ ኩባንያዎቻቸው ጋር በተያያዘ ከዚህ በፊት የተመሰረቱባቸውና ያልተዘጉ ሌሎች የፍርድ ቤት ክሶች እንዳሉባቸው የዘገበው ዩኤስ ቱዴይ በበኩሉ፣ ዶናልድ ትራምፕና የሚያስተዳድሯቸው ኩባንያዎች ባለፉት 30 አመታት ከ4ሺህ በላይ ክሶች እንደተመሰረቱባቸው አስታውሷል፡፡

የተጠቃሚዎቹ ቁጥር 1.79 ቢ. ደርሷል
     ታዋቂው የማህበራዊ ድረገጽ ፌስቡክ ባለፈው መስከረም በተጠናቀቀው የዘንድሮው ሶስተኛ ሩብ አመት 2.4 ቢሊዮን ዶላር ማትረፉንና 7.01 ቢሊዮን ዶላር አጠቃላይ ገቢ ማግኘቱን ባለፈው ሳምንት አስታወቀ፡፡
ፌስቡክ የሩብ አመት ትርፉ ካለፈው አመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ166 በመቶ እድገት በማሳየት 2.4 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን እንዳስታወቀ የዘገበው ስካይ ኒውስ፤ትርፋማ እንዲሆን ከፍተኛውን አስተዋጽኦ ያበረከተው ከሞባይል አገልግሎት ማስታወቂያ ያገኘው ገቢ መሆኑንም ጠቁሟል፡፡የፌስቡክ ተጠቃሚዎች ቁጥር 1.79 ቢሊዮን መድረሱን ያስታወቀው ኩባንያው፤ በሞባይል ብቻ ፌስቡክ የሚጠቀሙ ደምበኞቹ ቁጥርም 1.66 ሚሊዮን መድረሱን አመልክቷል፡፡
ኩባንያው በቀጣዩ አመት ኢንቨስትመንቱን በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያስፋፋ ማስታወቁንዘገባው ጠቅሶ፣ ከእነዚህ ኢንቨስትመንቶች መካከልም በድሮኖች አማካይነት ለገጠር አካባቢዎች የኢንተርኔት አገልግሎት ማዳረስ አንዱ እንደሆነ መጠቆሙን አስረድቷል፡፡

በዩክሬን የሚገኝ አንድ የኤሌክትሮኒክስ ኩባንያ መጠሪያ ስማቸውን አይፎን 7 ብለው ላስቀየሩ የመጀመሪያዎቹ አምስት ደምበኞቹ አዲሱን ስማርት ፎን፣አይፎን 7 እንደሚሸልም ባወጣው ማስታወቂያ መሰረት፣ የመጀመሪያው ወጣት ስሙን በይፋ ማስቀየሩን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
የ20 አመቱ ዩክሬናዊ ወላጆቹ ያወጡለትን ኦሌክሳንደር ቱሪን የተባለ ስም በአይፎን 7 መቀየሩን ባለፈው አርብ ማስታወቁን ተከትሎ፣ ኩባንያው ቃል የገባለትንና 850 ዶላር የሚያወጣውን አዲሱን የአፕል ምርት አይፎን 7 ስማርት ፎን ሸልሞታል ተብሏል፡፡ወጣቱ በሚመለከተው የአገሪቱ የህግ አካል ስሙን ለማስቀየር ወጪ ያደረገው 2 ዶላር ብቻ በመሆኑ ከተሸለመው አይፎን ዋጋ አንጻር አትራፊ ነው ብሏል ዘገባው፡፡
ዩክሬናዊው ለሽልማት ብሎ ያጸደቀውን አይፎን 7 የሚለውን አዲሱን ስሙን፣ ወደፊት ወደነበረበት በመቀየር በቀድሞ ስሙ ሊጠራ እንደሚችል መናገሩን የጠቆመው ዘገባው፤ ወጣቱ ስሙን መቀየሩ ቤተሰቦቹንና ጓደኞቹን አስደንግጧል ብሏል፡፡

  20ኛ ዓመቱን ለማክበር በዝግጅት ላይ የሚገኘው ወጋገን ባንክ፣ባለፈው ዓመት ባደረገው እንቅስቃሴ ከታክስ በፊት 478.5 ሚሊዮን ብር ማትረፉን አስታወቀ፡፡
ባንኩ ከትናንት በስቲያ ባካሄደው 23ኛ መደበኛና 12 ድንገተኛ ዓመታዊ የባለአክሲዮኖች ጉባዔ የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ አርአያ ገ/እግዚአብሔር ባቀረቡት ሪፖርት፣ አምና (2015/16) ባደረገው እንቅስቃሴ ታክስ፣ መጠባበቂያና ሌሎች ውጪዎች ከተቀነሰ በኋላ 375.6 ሚሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ ማግኘታቸውን ገልጸዋል፡፡
ለመንግሥት 102.9 ሚሊዮን ብር ግብር መክፈላቸውን፣ የተገኘው ትርፍ ከቀደመው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ6.6 በመቶ ብልጫ ማሳየቱንና ከእቅዱ 92 በመቶ ማሳካቱም ተጠቁሟል፡፡  
ካቻምና 1.5 ቢሊዮን ብር የነበረው የባንኩ የተከፈለ ካፒታል፣ አምና 1.8 ቢሊዮን ብር መድረሱንና ጠቅላላ ካፒታሉም ወደ 2.8 ቢሊዮን ብር ማደጉን ለማወቅ ተችሏል፡፡ የባንኩ ጠቅላላ ሀብት ካቻምና ከነበረው 13.7 ቢሊዮን ብር አምና ወደ 16.2 ቢሊዮን ብር ደርሷል፡፡ የተሰበሰበ ተቀማጭ ገንዘብ 11.8 ሚሊዮን ብር ሲሆን የመደበኛ ብድር መጠንም የግምጃ ቤት ሰነድ ግዢን ሳይጨምር 7.6 ቢሊዮን ብር እንደሆነ ተነግሯል፡፡
ባንኩ እ.ኤ.አ በ2025 በአፍሪካ ከሚገኙ 10 ስመጥርና ተፎካካሪ ባንኮች አንዱ የመሆን ራዕዩን ለማሳካት እየተጋ መሆኑን የጠቆሙት ፕሬዚዳንቱ፤ የደንበኞች አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል፣ የሰው ኃይል ብቃትን ለማጎልበት፣ የአገልግሎቱን ተደራሽነት ለማስፋትና የኢንፎሜሽን ቴክኖሉጂ አቅሙን ለማሳደግ እየሠራ ነው ብለዋል፡፡  
የባለአክሲዮኖች ቁጥር 2,456 የደረሰ ሲሆን ባንኩ በአሁኑ ሰዓት 3,385 ሠራተኞችን በሥሩ ያስተዳድራል፡፡ ወጋገን፤ ስታዲየም አካባቢ በማስገንባት ላይ ያለው ባለ 23 ፎቅ፣ ዘመናዊ የዋና መ/ቤት ሕንፃ፣75 በመቶ መጠናቀቁ ተጠቁሟል፡፡

 ቅዳሜ ጥቅምት 5 ቀን 2009 ዓ.ም በአዲስ አድማስ ጋዜጣ፤ “የጌዴኦ ዞን ከተሞች ነደዱ” በሚል ርዕስ የቀረበውን ዘገባ ይመለከታል፡፡ በመጀመሪያ በጌዴኦ ዞን በተከሰተ ግጭት ምክንያት በጠፋው የሰው ህይወትና በወደመው ንብረት የተሰማንን ጥልቅ ሀዘን እንገልፃለን፡፡
የተፈጠረውን ክስተት ተከትሎ ከላይ በተጠቀሰው ርዕስ የወጣው ዘገባ ሚዛናዊነት የጎደለው፣ የሌላውን ክብርና ዝና የሚነካ እንዲሁም በሀሰት የወነጀለና መረጃ በማዛበት ጭምር የቀረበ በመሆኑ በስህተት የተገለጹ የምንላቸውን እንደሚከተለው እናቀርባለን፤
ዲላ ከተማ ያሉ ባለአክሲዮኖች የከተማ መሬት እንደነበራቸውና የእነርሱ መሬት ላይ ጨፌ ዩኒየን እንደተሰጠ ተደርጎ የተዘገበው በፍጹም በተሳሳተ መረጃ ላይ የተመሰረተ ሲሆን ትክክለኛው መረጃ የሚከተለውን ይመስላል፡፡
የይርጋጨፌ ቡና ገበሬዎች ህብረት ሥራ ዩኒየን ኃ.የተ ሰኔ 14 ቀን 1994 ዓ.ም ተመስርቶ ነሐሴ 16 ቀን 1994 ዓ.ም ሕጋዊ ሰውነት ማረጋገጫ ያገኘ ድርጅት ነው፡፡ ዩኒየኑ በ1997 ዓ.ም የዲላ ማዘጋጃ ቤት፣ ባለሀብቶችና ማህበራት የከተማ ቦታ ወስደው እንዲያለሙ መጋበዙን ተከትሎ፣ ግንቦት 18 ቀን 1997 ዓ.ም የልማት ቦታ እንዲሰጠው ጥያቄ ቢያቀርብም  አፋጣኝ ምላሽ ባለማግኘቱ፣ በድጋሚ ታህሳስ 14 ቀን 1998 ዓ.ም ጥያቄ አቅርቧል፡፡ የቀረበውን ጥያቄ ተከትሎ በወቅቱ የኢንቨስትመንት መሬት ላይ ውሳኔ ይሰጥ የነበረው የዞኑ የሊዝ ኮሚቴ፣ ዩኒየኑን ጨምሮ ለስምንት (8) የተደራጁ አካላት በጥያቄያቸው መሰረት ቦታ በሰጠበት ወቅት ለዩኒየኑ 5,368 ካሬ ሜትር መጋቢት 9 ቀን 1998 ዓ.ም ወስኖ፣ ውሳኔው እንዲፈጸም መጋቢት 11 ቀን 1998 ዓ.ም በተጻፈ ደብዳቤ፣ ለዲላ ከተማ ማዘጋጃ ቤት አመራር በመስጠቱ፣ ማዘጋጃ ቤቱም በደብዳቤው መነሻ የካቲት 1 ቀን 1999 ዓ.ም በተጻፈ ደብዳቤ፣ “ለኢንቨስትመንት የወሰዱትን ቦታ የሊዝ ክፍያ ፈጽመው እንዲያለሙ ለማሳወቅ” በማለት የሊዝ ክፍያ ለዩኒየኑ ሲያሳውቅ፣ ዩኒየኑ የተጠየቀውን ገንዘብ ብር 146,000 (አንድ መቶ አርባ ስድስት ሺህ) በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዲላ ቅርንጫፍ፣ ገቢ አድርጓል፡፡
የሌሎች የነጋዴዎች ማህበራት ማለትም የሰባቱ ማህበራት ቦታ ተሰጥቷቸው ወደ ልማት የገቡ ቢሆንም ዩኒየኑ ቦታ ላይ ያረፉ የማ/ቤቱ ሱቆች ፈርሰው ቦታው ባለመጽዳቱ ከሦስት ዓመታት በላይ ለሆነ ጊዜ እንደሌሎቹ ማህበራት ወደ ልማት ሳይገባ ቆይቷል፡፡ አሁን ከዩኒየኑ ጋር ክርክር የገጠመው ማህበር ጥቅምት 10 ቀን 2001 ዓ.ም ሳሬንደም የገበያ ማህበር አክስዮን ማህበር በሚል ስያሜ ተመስርቶና የንግድ ፈቃድ ጥቅምት 16 ቀን 2001 ዓ.ም የኢንቨስትመንት ቦታ ጥያቄ ለዞኑ አስ/ጽ/ቤት ማቅረቡን ተከትሎ፣ ጽ/ቤቱም በበኩሉ ለዲላ ከተማ አስ/ጽ/ቤት ህዳር 17 ቀን 2004 ዓ.ም ድጋፍ እንዲደረግላቸው ደብዳቤ መጻፉን በፍ/ቤት ክርክር ወቅት ከነበረው የመረጃ ልውውጥ ለመረዳት ችለናል፡፡
ሆኖም የዞን አስ/ጽ/ቤት ቀደም ሲል ለሳሬንደም የገበያ ማዕከል አ/ማ እንዲያለሙት የድጋፍ ደብዳቤ የጻፈለት ቦታ ቀደም ሲል ለይርጋጨፌ ዩኒየን ተሰጥቶ የነበረ መሆኑን ማረጋገጡን በመግለጽ፣ ለአዲሶቹ አልሚዎች በአቅራቢያው ሌላ ቦታ እንዲፈለግ የካቲት 16 ቀን 2001 ዓ.ም ለዲላ ከተማ አስ/ጽ/ቤት በጻፈው ደብዳቤ አመራር ሰጥቷል። የከተማው የከንቲባ ጽ/ቤት ደግሞ የካቲት 17 ቀን 2001 ዓ.ም በተጻፈ ደብዳቤ፣ የከተማ መሬት ለሚያስተዳድረው ለዲላ ከተማ ማ/ቤት ከዞን አስ/ጽ/ቤት የተሰጠውን አመራር አስተላለፈ። የዲላ ማ/ቤት የተሰጠውን አመራር ወደ ጎን በመተው፣ ከዩኒየኑ ቦታ በመቁረስ፣ ጋይድ ማፕ በማዘጋጀት ሚያዚያ 20 ቀን 2001 ዓ.ም በተጻፈ ደብዳቤ የዩኒየኑን ቦታ ለሳሬንደም ለመስጠት የአፈጻጸም መመሪያ እንዲሰጠው የዲላ ከተማ አስተዳደርን ጠየቀ፡፡ ከተማ አስተዳደሩም ለማ/ቤቱ ካስተላለፈው አመራር የሚቃረን ጥያቄ ማስቆም ሲገባው፣ እንደአ መጣጡ ለዞኑ አስተዳደር ሲያስተላልፍ፣ የዞኑም አስተዳደር ጥያቄውን ተቀብሎ በማስተናገድ፣ ግንቦት 11 ቀን 2001 ዓ.ም አስቀድሞ ለዩኒየኑ የተሰጠውን ቦታ አሁን ደግሞ ለሳሬንደም በሚሰጥበት ሁኔታ በመስማማት ውሳኔ ሀሳብ አደራጅቶ፣ ለክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጽ/ቤት በጻፈው ደብዳቤ አቀረበ፡፡ በዚህ ወቅት ጉዳዩ ለክልል ርዕሰ መስተዳድር ጽ/ቤት የቀረበው፣ በክልሉ የመሬት አስተዳደር ላይ ችግር በመኖሩ ውሳኔ ይሰጥ የነበረው በክልል መስተዳድር ም/ቤት ነበር፡፡ የክልሉ ካቢኔ ሰኔ 26 እና 27 ቀን 2001 ዓ.ም ባካሄደው ስብሰባ፣ ቀደም ሲል በዞኑ የቀረበው የውሳኔ ሀሳብ፣ ቦታውን የማልማት መብት አስቀድሞ የተሰጠው ባለመብት መኖሩን የማያመላክት በመሆኑና የውሳኔ ሀሳቡ የቀረበው ደግሞ ከፍተኛ የመንግስትና የህዝብ ኃላፊነት ከተሰጠው የዞን አስ/ጽ/ቤት መሆኑን ከግንዛቤ በማስገባት፣ የቀረበውን የውሳኔ ሀሳብ ተቀብሎ በማጽደቅ ለተፈጻሚነቱ ሰኔ 29 ቀን 2001 ዓ.ም በተጻፈ ደብዳቤ ለዞኑ አስተዳደር አሳወቀ፡፡ ከዚህ በመቀጠል የዞኑ አስተዳደር ሐምሌ 2 ቀን 2001 ዓ.ም በተጻፈ ደብዳቤ ለከተማ አስ/ጽ/ቤት አመራር ሰጠ፡፡
ዩኒየኑም የማልማት መብት ባገኘበት ቦታ ላይ ሕገወጥ እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑን መረጃ ሲደርሰው፣ ሐምሌ 24 ቀን 2001 ዓ.ም ከተፈቀደለት ይዞታ እንዳይነካበት ማሳሰቢያ ደብዳቤ በመጻፍ፣ ቦታውም ጸድቶ ለልማት እንዲዘጋጅ እንዲደረግለት ጠየቀ፡፡ የሕገ ወጥ እንቅስቃሴ መረጃ የደረሰው የጌዴኦ ከተማ ልማት መምሪያ ሐምሌ 30 ቀን 2001 ዓ.ም በጻፈው ደብዳቤ፣ ማ/ቤቱ ከህገ ወጥ ተግባሩ እንዲቆጠብ አስጠነቀቀ፡፡ ይሁን እንጂ የመምሪያውን ተግሳጽ ለመስማት ማ/ቤቱ ዝግጁ አልነበረም፡፡ ይሁን እንጂ ዩኒየኑ ተስፋ ባለመቁረጥ አስተዳደራዊ ትኩረት እንዲሰጠው ተደጋጋሚ ጥረት አደረገ፡፡ በዚህ ሁሉ አቤቱታ መሃል ጥር 25 ቀን 2002 ዓ.ም ቦታው ከዩኒየኑ ተቆርሶ ለሳሬንደም መሰጠቱ ተሰማ፡፡ ከዚህ በኋላ አስተዳደራዊ መፍትሄ በመጥፋቱ ዩኒየኑ ጉዳዩን ወደ ጌዴኦ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመውሰድ ግንቦት 19 ቀን 2002 ዓ.ም በተላለፈው ውሳኔ ማ/ቤቱ፣ የዞኑን ሊዝ ኮሚቴው ውሳኔ በሕግ ተገድዶ እንዲፈጽም ታዘዘ። በዚሁ ውሳኔ ዩኒየኑ ከሦስት ዓመታት በፊት የሊዝ ክፍያ በፈጸመበት ሙሉ ይዞታ መጠን (5,368 ካሬ ሜትር) ላይ መብቱን በፍ/ቤት ውሳኔ አረጋገጠ፡፡ ከዚህ በመቀጠል ሰኔ 10 ቀን 2003 ዓ.ም በሙሉ ይዞታ ላይ (5,368 ካሬ ሜትር) ካርታ ተሰርቶ በመሰጠቱ ፍርዱ ተፈጸመ፡፡ በሕገ ወጥ መንገድ የተሰጠው የሳሬንደም ካርታ ሰኔ 15 ቀን 2003 ዓ.ም መሰረዙን ለሳሬንደም ለራሱና ለሌሎች የመንግሥት አካላት ተገለጸ፡፡
ከዚህ በኋላ ጉዳዩ ወደ ቀጣይ የክልልና የፌደራል ፍ/ቤቶች በሂደት አምርቶ፣ በመጨረሻም በፌደራሉ ጠ/ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ለተከራካሪው ወገን ተወሰነ፡፡ ጉዳዩ ወደ አፈጻጸም ክርክር ሲደርስ የመንግሥት ትኩረት አግኝቶ ክትትል ይደረግበት ስለነበር፣ ከዞኑ ከፍ/ቤት ጀምሮ እስከ ክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ጉዳዩ እንደ ፍርዱ መፈጸም የማይቻል በመሆኑ አማራጭ መንገድ በመከተል እልባት ሲሰጡ ቆይተው፣ የፌዴራል ሰበር ሰሚ ችሎት ግን የሥር ፍ/ቤት የአፈጻጸም ክርክር ላይ የሰጠውን ብይን መስከረም 23 ቀን 2009 ዓ.ም በዋለው ችሎት ሻረ፡፡
“ዩኒየኑ ፍርዱን በይሁንታ መቀበል አልቻለም፡፡ በዚህም ለበርካታ ሰዎች ህይወት መጥፋት፣ለበርካታ ንብረት ውድመት የዳረገው ግጭት እንደቀሰቀሰ ምንጮች ይናገራሉ” በሚል የቀረበው ፍጹም ሐሰትና ተራ ውንጀላ ነው፡፡
የይርጋ ጨፌ ቡና ገበሬዎች ኅብረት ሥራ ዩኒየን፣ በጌዴኦ ዞን በሚገኙ 27 ሁለገብ ኅ/ሥራ ማህበራት በታቀፉ ከ46,000 በላይ በሆኑ አርሶ አደሮች፣ በኢፌዴሪ ኅብረት ሥራ ማህበራት ማቋቋሚያ አዋጅ ከ14 ዓመታት በፊት የተቋቋመና በሀገር ልማትና ገጽታ ግንባታ የራሱን ከፍተኛ ሚና እየተወጣ ያለ ትልቅ ተቋም ነው፡፡ የዩኒየኑ ቦርድ፣ ማኔጅመንት እና ሰራተኞች ኃላፊነት የሚሰማቸውና የድሃውን አርሶ አደር ኑሮ ለማሻሻል ሌት ተቀን የሚታትሩ ከመሆናቸው የተነሳ፣ ለአልባሌ አስተሳሰብና ድርጊት ጊዜ የሌላቸውና ይህን የመሰለ አስከፊና ህገ ወጥ ድርጊት ለመፈፀም ተቋማዊ አጀንዳ አንግበው የሚንቀሳቀሱ አይደሉም፡፡ የቦታ ክርክሩንም ጉዳይ በተመለከተ በህጋዊ መንገድ ብቻ መፍትሄ እንደሚገኝ በመተማመን ሁሉንም ህጋዊ አማራጮች በሙሉ አሟጦ እየተጠቀመ ያለ ተቋም እንጂ በእንደዚህ ዓይነት ያልተገባ ድርጊት የመሳተፍ ፍላጎትም ሆነ ታሪክ የለውም፡፡ ስለዚህ ይህ መሰረተ ቢስ ውንጀላ ተገቢነት የሌላው በመሆኑ እንቃወማለን፡፡

ድምፃዊ ሔኖክ መሀሪ፤ ‹‹እውድሻለሁ›› በተሰኘው ዘፈኑ በ”ምርጥ የአር ኤንድ ቢ” እና የ”ሶል” አፍሪካዊ ድምፃዊ በመሆን፣ የ”ኦልአፍሪካ ሚዩዚክ አዋርድ” (አፍሪማ 2016) አሸናፊ ሆነ፡፡ ባለፈው እሁድ በናይጄሪያ ሌጎስ ከተማ በተካሄደው የሽልማት ስነስርዓት ላይ ሔኖክ ባሸነፈበት ዘርፍ 7 ታዋቂና ተፅዕኖ ፈጣሪ የናይጄሪያ ድምፃዊያን፣ ሁለት ደቡብ አፍሪካዊያን፣ አንድ ሩዋንዳዊና አንድ ማላዊ ድምፃዊያን ፉክክር አድርገው የነበረ ቢሆንም በመጨረሻ ሄኖክ ማሸነፉን ገልጾ፣ሆኖም አሸንፋለሁ ብሎ እንደላልጠበቀ ለአዲስ አድማስ ተናግሯል፡፡  
ጃኖ ባንድ ‹‹ዳሪኝ›› በተሰኘው ዘፈን፣ በ”ምርጥ ሮክ” እና “ምርጥ ቡድን”፣ ድምፃዊት ፍቅር አዲስ ነቅአጥበብ ደግሞ ‹‹ምስክር›› በተሰኘው ዘፈኗ፣”የምስራቅ አፍሪካ ምርጥ ሴት ድምፃዊት” እንዲሁም ድምፃዊ አንተነህ ምናሉ ‹‹ዋዮ›› በተሰኘው ዘፈኑ፣ “ተስፋ የተጣለበት ድምፃዊ” እና “ምርጥ የሬጌ አቀንቃኝ” በሚሉ ዘርፎች ታጭተው የነበረ ሲሆን ማሸነፍ ግን አልቻሉም፡፡
ውድድሩ 50 በመቶ በሙዚቃ ባለሙያ ዳኞች ነጥብ የሚሰጠው ሲሆን 50 በመቶው በህዝብ ምርጫ የሚገኝ ነጥብ መሆኑን የጠቆመው ድምፃዊ ሄኖክ፤ቅስቀሳ በተጀመረ ሰሞን ፌስቡክ መዘጋቱ ፈታኝ ቢሆንም ተስፋ ባለመቁረጥ በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ባደረገው ቅስቀሳና ዳኞች በሰጡት 50 በመቶ ነጥብ ማሸነፉ እንዳስደነገጠው አልደበቀም፡፡ ድምፃዊት ፀደንያ ገ/ማርቆስ ‹‹ሀርየት›› ለተሰኘው ፊልም በሰራቸው የማጀቢያ ሙዚቃ፣ባለፈው ዓመት (2015 አፍሪማ አዋርድ) “የምስራቅ አፍሪካ ምርጥ ሴት ድምፃዊት” በሚል ዘርፍ ማሸነፏ አይዘነጋም፡፡  
 በ34 የተለያዩ ዘርፎች አርቲስቶችንና የሙዚቃ ሥራዎቻቸውን አወዳድሮ አሸናፊዎችን ለሽልማት የሚያበቃው “አፍሪካ ሚዩዚክ አዋርድ”፤ በአህጉሪቱ ትልቁ ሽልማት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ የሽልማት ውድድሩ በየዓመቱ የሚካሄድ ሲሆን ዘንድሮ 2714 አፍሪካዊያን አርቲስቶች ተመዝግበው እንደነበረም ለማወቅ ተችሏል፡፡ በሌጎስ በተካሄደው በዚህ የሽልማት ስነስርዓት ላይ ከ2500 በላይ ጥሪ የተደረገላቸው የተለያዩ አፍሪካዊያን እንግዶች ታድመው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡

“እውነተኛ ለውጥ ነው የማመጣው … የኦባማ አይነት እንዳይመስላችሁ”

ማክሰኞ ማታ ወደ እንቅልፌ የሄድኩት ሄላሪ ክሊንተን እንደምትመረጥ እርግጠኛ ሆኜ ነበር። ጠዋት ባለቤቴ ትራምፕ እየመራ ነው ስትለኝ ደንብሬ ተነሳሁኝ፡፡ የደነበርኩት ጆሮዬን ማመን ስለተሳነኝ ነው፡፡ የምርጫውን ሂደት ስከታተል ነው የከረምኩት፡፡ ምንም እንደማይመለከተኝ አውቃለሁ፡፡ እኔ አፍሪካ ውስጥ እንጂ አሜሪካ ያለሁ ሰው አይደለሁም፡፡ በራሴ ሜዳ የምወክለው ሰው ስለሌለኝ በሌላ ሀገር ገብቼ እንደ መቀላወጥ ነው፡፡ ግን ህልም አለኝ፡፡ ሰው ነኝ፡፡ እንደ ማንኛውም ሰው ምርጫ አለኝ፡፡
ወደ ቴሌቪዥኑ ሄጄ ከቁርስ በፊት ተቀመጥኩኘ። ትራምፕ ድምፁን እየሰበሰበው ነው፡፡ ከእሱ ምርጫ ጣቢያና ከሂላሪ ምርጫ ጣቢያ ዘገባው እየተለዋወጠ ይሰራጫል፡፡ ከዘገባው ይበልጥ በሁለቱም ምርጫ ጣቢያ የተሰበሰቡ የደጋፊ ፊቶች፣ እየተከሰተ ስላለው ነገር እውነቱን ይናገራሉ፡፡ የሂላሪ ደጋፊዎች በማዘን ላይ ናቸው፡፡ በዲሞክራቶቹ ሀዘን እኔ መደሰት ጀመርኩኝ፡፡ ከዚህ ቀደም ሪፐብሊካንም ዲሞክራትም ሲመረጥ የምደግፈው አልነበረኝም። ግን ደግሞ ኦባማ ከዛሬ ስምንት ዓመት በፊት ሲመረጥ ደስተኛ ነበርኩኝ፡፡
ለኦባማ ስደግፍ ምክንያቴ ምን ነበር? … ግልፅ ነው፤ ጥቁር በመሆኑ ምክኒያት ብቻ ነበር፡፡ በብቃቱ አይደለም፡፡ ብቃቱ ለእኔ የቆዳ ቀለሙ ላይ የሚገኝ ይመስለኝ ነበር፤ መሳሳቴ እስኪገባኝ ስምንት ዓመት ማለፍ ነበረበት፡፡ የቀለም ዘረኛ ነበርኩኝ፤ ያኔ። ግን ፕሬዚዳንትነት ከቀለምም ሆነ ከድጋፍ ጋር ምንም ግንኙነት የለውም፡፡ እውነት ነው፤ ለምርጫ ምክኒያቱ፡፡ ኦባማ ታላቅ የንግግር ጥበብ አዋቂ ነው። ስምንት ዓመት በተለያየ መድረክ ላይ ሲናገር ተሰምቷል፡፡ ወደ ኢትዮጵያ መጥቶም ረጅም ንግግር ሲያደርግ ሰምቼዋለሁ፡፡ ግን ማውራት ነው እንጂ ሌላ ለውጥ አላመጣም፡፡
“Change we can” - የምርጫ መቀስቀሻው ሃረግ ነበረች፡፡ ለውጡ ወደ ምን እንደሆነ ግን አልታወቀም ነበር፡፡ አሁን ለይቷል፡፡ ቴሌቪዥኑ ላይ ማፍጠጤን ቀጠልኩኝ፡፡ የሂላሪ የምርጫ ውጤት 208 ላይ ቆሟል፡፡ የትራምፕ 245 ደረሰ። በጉጉት እየተጠበቀ ያለው የፔንስልቫኒያ እስቴት የምርጫ ድምፅ ነው፡፡ የሂላሪ የእድገት ግዛት ነው፡፡
ለእኔ የትራምፕ መመረጥ ምንድነው የሚፈይደው? ከሚለው ጥያቄ ጋር ተፋጠጥኩኝ። የሚፈይደው ነገርማ አለ፡፡ የአሜሪካ ፖለቲካ በአናቱ ከተዘቀዘቀ፣ የሀገሬም ፖለቲካ ቢያንስ ጥርሱ መውለቁ አይቀርም፡፡ የሀገሬ ፖለቲካ ከሂላሪ ፖለቲካ ጋር ብዙ ዝምድና አለው፡፡ የሂላሪ ፖለቲካ ከማንነት ፖለቲካ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ለሴቶች፣ ለብሄር ብሔረሰቦች፣ ለማይኖሪቲዎች .. ወደሚል አዝማሚያ ያጋደለ ነው፡፡ ክፍልፋይን የሚያበረታታ እንጂ ወደ አንድነት የሚያመራ አይደለም፡፡
በሂደት እንደተረዳሁት ሁሉም ፖለቲካ፣ ከኢኮኖሚ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ የፈለገ አይነት የፖለቲካ ጥያቄ ከማንነት ጥያቄ ይበልጥ የኢኮኖሚ መንስኤ ያለው ነው፡፡ ፍትሐዊ ሀብት የማፍራትና ፍትሀዊ የመከፋፈል ጉዳይ ነው … ሁሉም ጥያቄ ሲጠቃለል፡፡
ኦባማ ጥቁር መሆኑ ወይንም ሄላሪ ሴት መሆኑዋ ለኢኮኖሚ ኢ-ፍትሃዊነቱ መፍትሄ መሆን እስካልቻለ ድረስ የማንነት ጥያቄ አስፈላጊ አይደለም፡፡ መጀመሪያ የሰውነት ጥያቄ ነው፡፡
እንዲህ እያልኩ በማሰብ ውጤቱን መከታተል ቀጠልኩኝ፡፡ የሂላሪ ደጋፊዎች ከተቋም ጋር የተጋጩና ተቋሞችን በአጠቃላይ የሚጠሉ ስለመሆናቸው አንድ የኢኮኖሚ ባለሙያ ቀርቦ ሲናገር ሰማሁት፡፡ ባለሙያውን አውቀዋለሁ፡፡ በክሊንተን መንግስት ውስጥ የኢኮኖሚ አማካሪ ሆኖ ይሰራ የነበረ ሰው ነው፡፡
ሮበርት ራይሽ ይባላል። ለሮበርት ራይሽ መሰረታዊና ጤናማ ኢኮኖሚ፣ የመካከለኛ ገቢ የህብረተሰብ ክፍልን የሚያሳድግ ነው፡፡ መካከለኛ ገቢ ያላቸውን የሚፈጥር፣ የሚያጠነክርና የሚጠብቅ ስርዓት “ቅዱስ” ነው ብሎ ያምናል፡፡ ስለዚህ ምናልባት ህዝቡ ከተቋማቱ ጋር የተጣላው እነዚህ መብቶቹን የሚያስጠብቁ ስላልሆኑ ነው ብሎ ሀሳቡን ሰነዘረ፡፡ ሌሎችም ተራ በተራ እየተለዋወጡ የተለያዩ አስተያቶችን ይሰጣሉ። በአጠቃላይ ግን በቴሌቪዥን መስኮት የሚታዩት ሁሉ የደስታ ድባብ ውስጥ አልነበሩም፡፡  
በተለይ ምሁራኑ በተለያየ አቅጣጫ መበሳጨታቸውን እየገለፁ ነው፡፡ በቴሌቪዥን የሚታዩ ተንታኞች ግን ከህዝቡ ጋር ናቸው ወይንስ አይደሉም? አልኩኝ፡፡ ህዝብ ከተጣላው ተቋም ጋር ነው የሚሰሩት? … እሺ ምሁራንና ተንታኞቹስ ከተቋማቱ ጋር ያብሩ፤ ጋዜጠኞቹ ግን ምን ነክቷቸው ነው? … ለካ በፋውንዴሽን ታቅፈው ነው መረጃ የሚያጠናቅሩት፡፡ ከህዝቡ ጋር የቆመ ታዲያ ማነው? እንግዲህ ለህዝቡ የቆመው ማን እንደሆነ በግልፅ እየታየ ነው፡፡ ከህዝብ ፍላጎት ጋር የቆመው የምርጫ ሳጥኑ ብቻ ነበር፡፡ በምርጫ ሳጥኑ ውስጥ የተከማቸው ድምፅ ደግሞ የዶናልድ ትራምፕን ስም አጭቆ ይዟል፡፡
“Popular Vote” የሚል ነገር በቴሌቪዥኑ አንድ ጫፍ ተፅፏል፡፡ በ Popular Vote ላይ ያለው ቁጥር በሳጥኑ ውስጥ ካለው ይለያል፡፡ በጎዳና ላይ ወሬ ሂላሪ ተመርጣለች፡፡ በተጨባጩ የድምፅ መስጫ ሳጥን ውስጥ ግን የሴትየዋ ድምፅ ጎድሏል፡፡ በፕሮፓጋንዳ ምርጫ እሷ አሸንፋለች፡፡ እውነትና ፕሮፓጋንዳ ግን በህዝብና በተቋማት መሀል ያለውን ርቀት መልሰው ማንፀባረቃቸው የሚደንቅ አይደለም?
ከአንድ ወዳጄ ጋር ስለ ምርጫ ስናወራ የነገረኝ ቀልድ ትዝ አለኝ፡፡ በሰዎች መሀል ትራምፕን እንደሚደግፍ አንዱ የአሜሪካ ዜጋ ሲያወራ፣በዙሪያው ያሉ ሁሉ “እንትን የነካው እንጨት አደረጉት፡፡ “እንዴት እንደዚህ አይነት መሀይም፣ ዘረኛና ተሳዳቢ ሰው ትመርጣለህ?!” ብለው አዋከቡት፡፡ ግራ አጋቡት፡፡ ከከበበው ነቀፋ ለመራቅ ወጥቶ ሊሄድ ሲል ከታቃወሙት መሀል መሪ ሆኖ ሲጮህ የነበረው ከኋላው ተከትሎ በጆሮው፣ “እኔም ትራምፕን ነው የምመርጠው … ግን ሰው ፊት እንደዛ ብዬ አልናገርም … ሊያጠቁህ ይችላሉ” ብሎ ሹክ አለው፤ሲል አጫወተኝ፡፡ ከዚህች ቀልድ በላይ “Popular Vote”ን የገለጠልኝ ማስረጃ የለም፡፡ በቴሌቪዥኑ መስኮት የሪፐብሊካን የምርጫ ዘመቻ ዋና አቀናጁ፣ ጆን ፓዴስታ ብቅ ብሎ፣የሂላሪን ደጋፊዎች፤“ወደ ቤታችሁ ተመልሳችሁ ተኙ” ሲል ትዕዛዝ ሰጠ፡፡ ደጋፊዎቿ እያለቀሱ  ተበታተኑ፡፡
አሁን ትኩረት ሁሉ ወደ ሪፐብሊካኑ ጎራ ሆነ። እኔም የታሪክ አንድ አካል የመሆን ስሜት ለምን እንደተሰማኝ ማወቅ ፈልጌያለሁኝ፡፡ … ለምንድነው እኔም ፖለቲከኛ የምጠላው፡፡ ትራምፕ የቢዝነስ ሰው እንጂ ፖለቲከኛ አለመሆኑ ደጋግሞ ሲገለፅ ይሰማል። እንዲያውም ልሂቃን ከሚባሉት ጋር እንደማይቆም ይነገራል፡፡ “የአሜሪካ ህዝብ በአብዛኛው እኮ መሀይም ነው … ትራምፕን ቢደግፉ አይግረምህ፤ እንደ አውሮፓ ህዝብ ጥልቅ ነገር አይገባውም” ያለኝ አንድ ምሁር ትዝ አለኝ፡፡ አሁን ትራምፕ ሊመረጥ መሆኑን ሲሰማ ምን ይል ይሆን? ስል አሰብኩኝ፡፡
በእርግጥ ግን ዲሞክራሲና እውቀት ምንና ምን ናቸው፡፡ መሀይም ህዝብ፤ የሚፈልገውን መሪ አያቅም ማለት ነው? … አንድን ብቁ የሚለውን ሰው ለመምረጥ ሰው መሆን ብቻ በቂ አይደለም እንዴ? የፖለቲካ ውድድር በእርግጥ የኦሎምፒክ ውድድር አይደለም፡፡ አንድ ማራቶን ውድድር ላይ ተካፍሎ ያሸነፈውን ለማወቅ፣ ምርጫና ክርክር አያስፈልገውም፡፡ ግልፅ ነው፡፡ የሰው ብቃት በአካል ተገልፆ ሲታይ ክርክር አይፈጥርም፡፡
አንድ የምርጫ እጩ ለህዝቡ የሚሆን እውነትን ሲያቀርብስ? … አዎ ያከራክራል፡፡ ስለሚያከራክር ነው የድምፅ ብልጫ ያስፈለገው፡፡ ድምፁን በምርጫ ሳጥን ከቶ መቁጠር ያስፈለገው ክርክሩን ለመክፈል ነው፡፡ ህዝብ የሚመርጠውን አያውቅም ከተባለ ዲሞክራሲ የማይሰራ ፅንሰ ሀሳብ ነው እንደ ማለት ነው፡፡
መሀይም ቢሆንም ተመረጠ፡፡ የተሰበሰበው ህዝብ በጩኸት ደስታውን ገለፀ፡፡ የሚዲያ ተቋማቱ “የተከሰተው የፖለቲካ ስርዓት መሬት መንቀጥቀጥ ነው” ይላሉ ደጋግመው፡፡ ልክ ፀሐይ በምዕራብ የወጣች ይመስላል እንዲህ ሲሉ። መገረማቸው የመነጨው ከትምክህታቸው መሰለኝ። የማያውቁትን ህዝብ እናውቀዋለን ብለው ደመደሙ፡፡ ድምዳሜው ስህተት መሆኑ ሲገለፅ የሚሰጥ ትንታኔ ማቅረብ ጀመሩ፡፡
ከዚህ ቀደም መሀይምነትን ከሀይማኖተኛ ፅንፈኝነት ጋር በማያያዝ ነበር ትንታኔ የሚሰጡት፡፡ ወይንም “ካፒታሊዝምን ሊያፈርስ የመጣ ኮሚኒስት ነው” በማለት ነበር የሚወነጅሉት፡፡ ግን ንግድን የሚያበረታታ ፅንፈኛ ወይንም ታክስን እቀንሳለሁ የሚል ኮሚኒስት ለሀሜት አይመችም፡፡ ከዚህ ቀደም የቡሽ አስተዳደር ያማረራቸው ሪፐብሊካኖች (ያውም ቀይ አንገት ነጮች) ጥቁሩን ኦባማን በአንድ ድምፅ መርጠውታል፡፡ አሁን ደግሞ ጥቁሩ ሰው የሚፈልጉትን አልሰማ ሲል ለወጡት፡፡ ምንም ፍረጃ አያስፈልገውም፡፡ ከፑቲን ጋር ለመስራት መፈለጉም የህዝቡን ድምጽ አላሳጣውም፡፡  
… ብቻ ውጤቱ ታወቀ፡፡ ትራምፕ በከፍተኛ (278) ድምጽ ተመረጠ፡፡ ሂላሪ ስታለቅስ ቆይታ ደጋፊዎቿን ለማሰናበት መጣች፤ “ዋናው አሜሪካ ናት … ከትራምፕ ጋር መስራት አለብን” አለች፡፡ ዶናልድ ማሸነፉን ሲያውቅ ለደጋፊዎቹ ያደረገውን ንግግር ተሸናፊዋም ደገመችው፡፡ ልዩነትን መግጠም ላይ አተኮሩ፡፡ ስንጥቁ ግን በቀላሉ የሚገጥም አይመስልም፡፡ ኦባማም ብቅ ብሎ፣ከወዲሁ የሽግግር ሂደቱን አቀላጥፎ፣ ለዶናልድ ስልጣኑን ለማስረከብ እንደጓጓ ተናገረ፡፡
ቀኑን ሙሉ ቴሌቪዥን ላይ የተከልኩትን አይኔን ነቀልኩኝ፡፡ ትራምፕን ከክርክሩ ጀምሮ እደግፈው ነበር፡፡ ድጋፌ የመነጨው እውነትን የሚናገር መስሎ ስለተሰማኝ ነው፡፡ የሚመስል ሁሉ አይሆንም የሚሉኝ ብዙ ናቸው፡፡ መምሰል መጀመር ራሱ ትልቅ ነገር ነው፡፡ ወደ መሆን እና ወደ ለውጥ የመጓዣ ብቸኛው መንገድ ነው፡፡
“እውነተኛ ለውጥ ነው የማመጣው … የኦባማ አይነት ለውጥ እንዳይመስላችሁ” ብሏል፤ ሰውየው።
የምርጫ ውድድሩ የመጀመሪያ ሂደት ላይ … ገና የሪፐብሊካን እጩ ለመሆን በመወዳደር ላይ ሳሉ አንድ የጋዜጣ አምደኛ፤ “ትራምፕ የሪፐብሊካን ፓርቲ እጩ ሆኖ ከተመረጠ የምፅፍበትን የጋዜጣ አምድ እበላዋለሁ …” ብሎ ፎክሮ ነበር፡፡
እንግዲህ ከእጩነት አልፎ ሰውየው ፕሬዚዳንት ሆነ፡፡ የጋዜጣ አምዱን ቀርቶ የህገ መንግስቱን ድርሳን በአጠቃላይ እየቀደደ ቢበላውም ይህ ሁነት የሚለወጥ አይሆንም፡፡

    በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ ስደተኞች የሰብዓዊ ድጋፍ ይፈልጋሉ
በየመን የሚገኙ በመቶዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች የጦርነትና የአየር ድብደባዎች ሰለባ ሊሆኑ በሚችሉበት እጅግ አደገኛ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኙ የአለማቀፉ የስደተኞች ድርጅት ትናንት ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
በየመን የተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች፤ የሰብዓዊ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው የጠቆመው መግለጫው፣ ድርጅቱ በየመን በሚካሄዱ የአየር ጥቃቶችና የምድር ጦርነቶች ሳቢያ አቋርጦት የነበረውን ስደተኞችን ወደአገራቸው የመመለስ ስራ እንደገና መጀመሩንም አስታውቋል፡፡
የድርጅቱ የጅቡቲ፣ የኢትዮጵያና የየመን ቢሮዎች በጋራ ባደረጉት እንቅስቃሴ፤ ሆዴዳ በተባለው የየመን አካባቢ የነበሩ 672 ስደተኞችን ከአካባቢው የማስወጣት ስራ መስራታቸውን የጠቆመው መግለጫው፣ ተጨማሪ 150 ስደተኞችም በትናንትናው ዕለት ጅቡቲ ይደርሳሉ ተብሎ እንደሚጠበቅና ወደ ኢትዮጵያ እንዲመለሱ እንደሚደረግ ገልጿል፡፡

የጸረ-ትራምፕ ተቃውሞው ከ27 በላይ ከተሞችን አዳርሷል
    በዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ሪፐብሊካኑን ወክለው የተወዳደሩት ዶናልድ ትራምፕ ማሸነፋቸውን የሚገልጸው የምርጫ ውጤት ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ባለፈው ረቡዕ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ተባብሶ መቀጠሉ እየተዘገበ ነው፡፡
የትራምፕን በምርጫ ማሸነፍ በመቃወም ወደ አደባባይ የወጡ ተቃዋሚዎች በአስር ሺህዎች እንደሚቆጠሩ የዘገበው ሲኤንኤን፤ ረቡዕ ዕለት የተጀመረው ተቃውሞ ወደ በርካታ የአገሪቱ አካባቢዎች መዛመቱንና እስከ ሃሙስ ድረስም ከ25 በላይ በሚሆኑ የአገሪቱ ከተሞች ተቃውሞ መደረጉን ጠቁሟል፡፡
ተቃዋሚዎቹ ትራምፕ ስልጣን መያዛቸው አግባብ አለመሆኑንና አገር የመምራት ብቃት እንደሌላቸው በመግለጽ፣ ፎቶግራፋቸውን ከማቃጠልና በተለያዩ ተቋማት ላይ ጥፋት ከማድረስ አልፈው በአንዳንድ የአገሪቱ አካባቢዎችም የምርጫ ውጤቱ እንዲሰረዝና ሄላሪ ክሊንተን ስልጣን እንዲይዙ እስከመጠየቅ መዝለቃቸውን ዘ ጋርዲያን ትናንት ዘግቧል፡፡
ረቡዕ የጀመረው ተቃውሞ ሃሙስም ወደ ዴንቨር፣ ሚኒያፖሊስ፣ ፖርትላንድ፣ ኦክላንድና ሌሎች የአሜሪካ ከተሞች መስፋፋቱን የዘገበው ዘ ጋርዲያን፣ በፖርትላንድ 4 ሺህ ያህል ተቃዋሚዎች አደባባይ በመውጣት በፖሊስ መኮንኖችና በመደብሮች ላይ ጥቃት መፈጸማቸውንና ፖሊስም ከ29 በላይ ሰዎችን ማሰሩን ገልጧል፡፡
በዴንቨርም 3 ሺህ ያህል አሜሪካውያን ተቃውሞ ማድረጋቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ አሜሪካውያን በቀጣይም ተቃውሟቸውን ለመቀጠልና የትራምፕን አሸናፊነት እንደማይቀበሉ የሚገልጹ ድርጊቶችን ለመፈጸም እያቀዱ ነው ሲል ዘ ጋርዲያን ትናንት ዘግቧል፡፡
በዋሽንግተን ሰፋ ያለ ተቃውሞ ለማድረግ ታስቦ በፌስቡክ የተከፈተው ዘመቻ እስከ ሃሙስ ተሲያት ድረስ፣ 30 ሺህ አባላትን ማፍራቱን የጠቆመው ዘገባው፤ ተቃውሞውን የሚደግፉ የቡድኑ አባላት ቁጥር በየሰዓቱ በሺህዎች እያደገ እንደሚገኝ አስታውቋል፡፡
አሜሪካ በትራምፕ አሸናፊነት በተከፉ ተቃዋሚዎች ብትጥለቀለቅም፣ በምርጫ ቅስቀሳው ወቅት አንዳቸው ሌላኛቸውን ሲያብጠለጥሉና ሲወነጅሉ የከረሙት ተመራጩ ዶናልድ ትራምፕና ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ግን፣ ሃሙስ በዋይት ሃውስ ተገናኝተው ልዩነትን ያሸነፈ ውይይት አድርገዋል ተብሏል፡፡
ኦባማና ትራምፕ 90 ደቂቃ በፈጀው ውይይታቸው፤ ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር በሚደረግበት ሁኔታና በሌሎች ብሄራዊና የውጭ ጉዳይ ፖሊሲዎች ዙሪያ መምከራቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡