Administrator

Administrator

   በህፃናት አመጋገብ ዙሪያ በጥናት ላይ ተመስርቶ ያዘጋጃቸውን ማኑዋሎች ሰሞኑን ለባለድርሻ አካላት ይፋ ያደረገው  ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ፤ በስልጠና ማኑዋሎቹ አማካኝነት ሰፊ ለውጥ ይመጣል ተብሎ እንደሚጠበቅ አስታውቋል። በተለይ ህፃናት ተወልደው 1 ሺህ ቀናት ድረስ ባሉት ጊዜያት ያለው አመጋገባቸው ለእድገታቸው ወሳኝ መሆኑን በተመለከተ በኦሮሚያ ክልል ሁለት ወረዳዎች በወላጆችና ህፃናት ላይ ውጤታማነቱን ማረጋገጥ እንደተቻለ የጠቆመው ወርልድ ቪዥን፤ ለጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ተወካዮችና በህፃናት ላይ ለሚሰሩ መንግስታዊ ላልሆኑ ድርጅቶች፣ከትላንት በስቲያ በሳርማሪያ ሆቴል  ስልጠና ሰጥቷል፡፡
በስልጠናው ላይ በቀረበው ጥናታዊ ፅሁፍ፤ በሁለቱ ወረዳዎች በተለይ የህፃናት አመጋገብን አስመልክቶ በቤተሰብ ግንዛቤ ላይ በተሰራ ስራ፣ አመርቂ ውጤቶች መምጣታቸው የተገለጸ ሲሆን ይህንን የግንዛቤ ስራ ወደ አገር አቀፍ ደረጃ በማሳደግ፣ ህፃናትን ከመቀንጨር በመከላከል፣ በቂ ክብደት ኖሯቸው እንዲያድጉ በማድረግ፣ ምርታማ ዜጋን ለማፍራት አማራጭ የሌለው መፍትሄ ነው ብለዋል - በወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ፣ የፕሮግራም ውጤታማነትና የማስተማር ስትራቴጂ ዳይሬክተር አቶ በየነ ገለታ፡፡ አዲሱ የስልጠና ማንዋል በተለይ ለጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ግብአት በመሆን፣ በአገር አቀፍ ደረጃ አገልግሎት ላይ እንደሚውልም ዳይሬክተሩ አክለው ገልጸዋል፡፡
ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ወደ 55 በሚጠጉ ወረዳዎች በአገር አቀፍ ደረጃ እንደሚሰራ የገለፁት ዳይሬክተሩ፤ ትኩረቱንም በጤና፤ በትምህርት፣ በማህበረሰብ ልማትና በምግብ ዋስትና ላይ እንደሚያደርግ ተናግረዋል፡፡
በወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ የኒዩትሪሽን ዲፓርትመንት ቴክኒካል ሀላፊ አቶ በኩረፅዮን አሳሳኸኝ በበኩላቸው፤ ይህንን የህፃናት አመጋገብ በማስተካክል በኩል ዋናው ተዋናይ መንግስት ቢሆንም ወርልድ ቪዥን የጥናት ውጤቶችን ለመንግስት በማቅረብ የበኩሉን እንደሚወጣ ገልፀዋል፡፡
በአንዳንድ አካባቢዎች በምግብ እጥረት፣በሌላ አካባቢ በግንዛቤ እጥረት፣ ልጆች ከህፃንነታቸው ጀምሮ ሁለት ዓመት እስኪሞላቸው ድረስ ባለው ጊዜ የተመጣጠነ ምግብ እንደማያገኙ ጥናቱ በተደረገባቸው ሁለት ወረዳዎች መረጋገጡን የጠቆሙት አቶ በኩረፅዮን፤ በጥናቱ ወቅት ግንዛቤ ያገኙ ወላጆች፣ አመጋገብ ላይ በሠሩት ስራ አመርቂ ውጤት መምጣቱንና በስልጠና ማኑዋሎቹ በስፋት ለውጥ ይመጣል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል፡፡

ከእያንዳንዱ ጠርሙስ ውሃ፣ 1ሣንቲም፣ ለችግረኞች ድጋፍ ይውላል

ዋው የማዕድን ውሃ ፋብሪካ ምርት ከጀመረበት ቀን አንስቶ ከሸጣቸው ከእያንዳንዱ ጠርሙስ የማዕድን ውሃ ላይ አንድ ሳንቲም፣ ጧሪና ደጋፊ ለሌላቸው አረጋውያንና ወላጆቻቸውን ላጡ ህፃናት ድጋፍ አደረገ፡፡ ድርጅቱ ያደረገው የገንዘብ ድጋፍ፤ ቀጣይነት ያለውና ቋሚ
መሆኑን የፋብሪካው ባለቤትና ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ጠንክር በቀለ ገልፀዋል፡፡ ሰሞኑን በጉራጌ ዞን ቸአ ወረዳ ውስጥ በሚገኘው
የፋብሪካው ቅፅር ግቢ በተከናወነ ሥነሥርዓት፣ድርጅቱ 60 ለሚሆኑ አረጋውያንና ችግረኛ ህፃናት የገንዘብ ድጋፍ አድርጓል፡፡ በአረጋውያኑና በህፃናቱ ስም በንብ ኢንተርናሽናል ባንክ በተከፈተ የቁጠባ ሂሳብ፣ ለእያንዳንዳቸው 1500 ብር ገቢ የተደረገላቸው ሲሆን ችግረኞቹን በዘላቂነት ለመደገፍ ድርጅቱ ቃል ገብቷል። ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ ባደረጉት ንግግርም፤የተደረገው የገንዘብ ድጋፍ፣ ድርጅቱ የገባውን ቃል
የሚያረጋግጥበትና ሃገራዊ ሃላፊነቱን በመወጣት ተግባራዊ እንቅስቃሴውን የሚያሳይበት ነው ብለዋል፡፡ ድጋፍ የተደረገላቸው አረጋውያንና ወላጅ
የሌላቸው ህፃናት በበኩላቸው፤ ባገኙት ድጋፍ ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸው፣ ድርጅቱ በቀጣይነት በሚያደርግላቸው ድጋፍ፣ ህይወታቸውን ለማስተካከል የሚችሉበትን ሥራ ለመስራት እንደሚጥሩ ተናግረዋል። በዕለቱ በፋብሪካው ቅጥር ግቢ ውስጥ የተገኙ በርካታ
የአካባቢው ተወላጅ ባለሃብቶችም፣ለችግርኛ ህፃናቱና አረጋውያኑ የተለያዩ ድጋፎችን አድርገዋል፡፡ በ”የካብዲ አግሮፕሮሰሲንግ” ኃ.የተ.የግ.ማ ሥር
የተቋቋመው ዋው የማዕድን ውሃ ፋብሪካ፤ ለአካባቢው ወጣቶች የሥራ ዕድል በመፍጠርና ሌሎች አገር አቀፍ ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞችን በማስገኘት ሰፊ እንቅስቃሴ እያደረገ እንደሚገኝ የገለፁት የፋብሪካው ባለቤት፤ ከዚህ ባሻገር ችግረኛ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን በቋሚነት ለመደገፍ ዕቅድ ነድፎ በስፋት እንደሚንቀሳቀስ ተናግረዋል፡፡ ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ካፒታል የተቋቋመው ድርጅቱ፤ በቀጣይ በወተትና የወተት ተዋፅኦ፣ በፍራፍሬ ጭማቂዎችና በሌሎች የምግብና የመጠጥ አግሮፕሮሰሲንግ ሥራዎች ላይ በስፋት እንደሚሰማራ አቶ ጠንክር ገልፀዋል፡፡

“የተሻለ ኮንስትራክሽን፣ ለተሻለች ኢትዮጵያ”


የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ሥራ ተቋራጮች ማህበር በየዓመቱ የሚያዘጋጀው “ኢትዮ ኮን” ዓለም አቀፍ የኮንስትራክሽን ኤግዚቢሽን ባለፈው ረቡዕ በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል የተከፈተ ሲሆን ነገ አመሻሽ ላይ ይጠናቀቃል ተብሏል። “የተሻለ ኮንስትራክሽን፣ ለተሻለች ኢትዮጵያ” በሚል መሪ ቃል በተከፈተው በዚህ ኤግዚቢሽን ላይ ከ100 በላይ የአገር ውስጥና የውጭ የኮንስትራክሽን ኩባንያዎች የተሳተፉ ሲሆን ከውጭዎቹ ሀገራት፡- ቻይና ቱርክ፣ ህንድ፣ ደቡብ ኮሪያና ሌሎችም ተሳታፊ መሆናቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በኤግዚቢሽኑ ላይ የኮንስትራክሽን እቃ አምራቾች፣ አቅራቢዎች፣ ዲዛይንና ስፔስፊኬሽን አዘጋጆች፣ ስራ ተቋራጮች፣ የሪል እስቴት አልሚዎች፣ ኤጀንቶች፣ የኮንስትራክሽን ማሽነሪ የአገር ውስጥ አምራቾች፣ አስመጭና አከፋፋዮች እንዲሁም ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል፡፡
የኢትዮጵያ የኮንስትራክሽን ሥራ ተቋራጮች ማህበር ፕሬዚዳንት ኢ/ር አበራ በቀለ በመክፈቻው ላይ ባደረጉት ንግግር፤ በኢትዮጵያ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ የመጣው የኮንስትራክሽን ዘርፍ፣ እድገቱ ጤናማና ትክክለኛ እንዲሆን ለማድረግ፣ ሀላፊነቱ የዘርፉ ባለድርሻ አካላት ቢሆንም በዋናነት ከዘርፉ ባለቤት ከኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ብዙ እንደሚጠበቅ ጠቁመው፣ አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ኤግዚቢሽኑ ምርትና አገልግሎትን ለጎብኚ በማቅረብ ብቻ ሳይወሰን የውይይት መድረክም አዘጋጅቷል፡፡ በዛሬው ዕለት ከጠዋቱ 2፡30 ጀምሮ በኢሲኤ አዳራሽ፤ “ወቅታዊ የኢትዮጵያ የኮንስትራክሽን ሥራ ተቋራጮች ተግዳሮቶችና የእድገት ማነቆዎች”፣ “የቴክኖሎጂ ሽግግር በካፒታል ኢንተንሲቭ፣ በኮንስትራክሽን ዘዴ”፣ “የኮንስትራክሽን ግዢና የኮንስትራክሽን አስተዳደር”፣ “ብክነትና ሊን ኮንስትራክሽን” በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ጥናታዊ ፅሁፎች ቀርበው  ውይይት እንደሚካሄድ ለማወቅ ተችሏል፡፡

አዲስ አበባ የጤናና የቢዝነስ ኮሌጅ፣ ለ13ኛ ጊዜ በዲግሪና በደረጃ አራት ያሰለጠናቸውን 429 ተማሪዎች ባለፈው ሳምንት በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ አስመረቀ።ተመራቂዎቹ በነርሲንግ፣ በጤና መኮንን፣ በክሊኒካል ነርሲንግና በላብራቶሪ ቴክኒሺያን የትምህርት ዘርፍ
የሰለጠኑ እንደሆኑ ታውቋል፡፡ኮሌጁ ከተመሰረተበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን ድረስ በሶማሌ ላንድ ሀርጌሳ የሚገኘውን ካምፓስ ጨምሮ
በአዲስ አበባና በተለያዩ ክልሎች ባሉት ካምፓሶቹ፣ከ47ሺህ በላይ የህክምና ባለሙያዎችን አሰልጥኖ በማስመረቅ በጤናው ዘርፍ ያለውን የባለሙያ ክፍተት ሲሞላ መቆየቱን የኮሌጁ ባለቤትና ፕሬዚዳንት ተናግረዋል፡፡ ከተመረቁ 47 ሺህ ባለሙያዎች መካከል
ከ10 ሺህ በላይ የሚሆኑት በኮሌጁ ነፃ የትምህርት እድል ተጠቃሚዎች እንደነበሩ ያስታወሱት ፕሬዚዳንቱ፤
በየካምፓሶቹ በዓመት ለ20 ተማሪዎች ነፃ የትምህርት እድል እንደሚሰጥና በተለይ መክፈል ባለመቻል መማር ላልቻሉ ሴት ልጆች ቅድሚያ በመስጠት ኃላፊነቱን ሲወጣ እንደቆዩ አክለው ገልፀዋል፡፡ተማሪዎች እዚህ ትምህርታቸውን አጠናቅቀው ለከፍተኛ ትምህርት አሜሪካ በሚሄዱበት ወቅት ተቀባይነት የሚያስገኝ፣ በአሜሪካ እውቅና ያለው ብቸኛ ኢትዮጵያዊ ኮሌጅ መሆኑን ፕሬዚዳንቱ በምርቃቱ ዕለት አስታውቀዋል

በብርሀኑ ደጀኔ የተሰናዳውና በእውነተኛ ታሪኮች ላይ ያጠነጥናል የተባለው፣ “በራስ እይታ የእማዬ ውለታ” መፅሀፍ ለንባብ በቃ።መፅሀፉ፤ የልጅነት፣ የስራ፣ የት/ቤትና ተለያዩ የህይወት አጋጣሚዎችን ያስቃኛል፤ ተብሏል። በ74 ገጽ የተመጠነው መፅሀፉ፣ በ70 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

Monday, 25 September 2017 11:56

የዒላማ ግርዶሽ

ርዕስ የለሽ ጽሕፈት
ውል አልባ ምዕራፍ
የምገርፈው በሬ
የሚጮኸው ጅራፍ
ያገር ደጅ ስጠና
ተከፈተ በራፍ፡፡
ክፋት ላይ ስተኩስ
ቅንነት ተመታች
ለተኩላ ባለምኩት
እርግብ በ’ራ ገባች
እርኩስ መቺ ቀስቴ
ደግ ላይ ተሰካች፡፡
ባላሚ ታላሚ
መሀል ስቶ ገብቶ
የዒላማ ግርዶሽ
ባገር ተንሰራፍቶ
አልሞ ለመምታት
አልተቻለም ከቶ፡፡
ከምሥጋና ጋር
ሳምሶን ጌታቸው ተ/ሥላሴ

* የቅዱስ ላሊበላ ደብርንና የደብረ ሊባኖስ ገዳምን ይጐበኛሉ
* ከፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ ጋር እንደሚነጋገሩ ይጠበቃል

     የሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ቅዱስ ባስልዮስ ማር ቶማ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ የፊታችን ማክሰኞ በሚከበረው የመስቀል ደመራ በዓል ላይ ለመገኘት ከነገ በስቲያ ቀትር ላይ አዲስ አበባ የሚገቡ ሲሆን ከርእሰ ብሔሩ ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ ጋራ ተገናኝተው እንደሚነጋገሩ ተጠቁሟል፡፡
ቅዱስ ፓትርያርኩ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን አምስት ልኡካን በመምራትም፣ በኢትዮጵያ የአራት ቀናት ጉብኝት እንደሚያደርጉ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡
ለጉብኝቱ በወጣው መርሐ ግብር መሠረት፥ ሰኞ፣ ከቀትር በኋላ፣ የህንዱ ፓትርያርክ፣ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ኦፌሴላዊ አቀባበል ይደረግላቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱና የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ሊቃውንት፣ የሰንበት ት/ቤት አባላትና ምእመናን በተገኙበት በሚደረገው አቀባበል፣ ፓትርያርኩ፣ ትምህርተ ወንጌል ይሰጣሉ፤ ተብሏል፡፡
በማግሥቱ ማክሰኞ፣ ከርእሰ ብሔሩ ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ ጋራ ተገናኝተው እንደሚነጋገሩ የተጠቀሰ ሲሆን፤ ከቀትር በኋላም፣ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ጋራ ወደ መስቀል ዐደባባይ በማምራት፣ የደመራን በዓል ያከብራሉ፡፡ ብዙ ሺሕ የሰንበት ት/ቤቶች ወጣቶች የሚያቀርቡትንና የሥነ በዓሉ ድምቀት የሆነውን ዐውደ ትርኢት የሚመለከቱት የህንዱ ፓትርያርክ፤ የሁለቱን አገሮችና አብያተ ክርስቲያናት ጥንታዊ ወዳጅነትና ቀጣይ ግንኙነት የተመለከተ ንግግር የሚያደርጉ ሲሆን ደመራውን፣ ከፓትርያርክ አቡነ ማትያስና ከአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ድሪባ ኩማ ጋራ በአንድነት እንደሚለኩሱ ተጠቁሟል፡፡
በዕለተ ረቡዕ የመስቀል በዓልን፣ በላሊበላ ደብር ውቅር አብያተ ክርስቲያናት በመገኘት እንደሚያከብሩም የተገለጸ ሲሆን ከዚያም መልስ፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ቤተ መጻሕፍት ወመዘክርን፣ የሰበታ ጌቴሰማኔ ቤተ ደናግል ሴቶች ገዳምንና የደብረ ሊባኖስ ገዳምን እንደሚጎበኙ መርሐ ግብሩ ያስረዳል። ከጉብኝታቸው ፍጻሜ በኋላ፣ በሁለቱ እኅትማማች አብያተ ክርስቲያናት አንድነትና ዓለም አቀፍ አገልግሎት ዙሪያ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ ደረጃ የጋራ ምክክር እንደሚያካሒዱና መግለጫም እንደሚሰጡ ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ ባለፈው ዓመት ኅዳር ሕንድን በጎበኙበት ወቅት ባቀረቡላቸው ግብዣ መሠረት፣ መስቀል ደመራን በኢትዮጵያ የሚያከብሩት ቅዱስ ባስልዮስ ማር ቶማ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ ለመጀመሪያ ጊዜ ከተገኙበት የካቲት ወር 2005 ዓ.ም. በዓለ ሢመት ወዲህ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ የሚያደርጉት ጉብኝት እንደሆነና የሁለቱን አብያተ ክርስቲያናት የተጠናከረ ግንኙነት እንደሚያሳይ ተጠቅሷል፡፡
ከቀድሞም ጀምሮ በአገራችን ዘመናዊ ትምህርት ቤቶች ጎልቶ የሚታየው የሕንዳውያን መምህራን አገልግሎት፣ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሥነ መለኰት ኮሌጆችም መኖሩን ምንጮቹ አስገንዝበዋል፡፡ በአንጋፋው የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በማስተማር የሚታወቁ ዕውቅ የሥነ መለኰት ሊቃውንትን ያወሱት ምንጮቹ፤ ኮሌጁ በቀድሞው መንግሥት ተዘግቶ ዳግም ከተከፈተበት ከ1987 ዓ.ም. ወዲህም አገልግሎታቸው መቀጠሉንና ከመምህራኑም  መካከል ለማዕርገ ጵጵስና የበቁ እንዳሉ ጠቅሰዋል። ይህም፣ የቆየውን ግንኙነትና ትብብር ለማጠናከር ከፍተኛ ሚና መጫወቱን አስረድተዋል፡፡
ቅዱስ ባስልዮስ ማር ቶማ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ እ.ኤ.አ ከኖቨምበር 2010 ጀምሮ፣ በሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ቶማስ የተሠየሙ 91ኛው የምሥራቅ ካቶሊኮስና የማላንካራ መጥሮጶሊጣን ናቸው፡፡ በኦፊሴላዊ ስያሜዋ፣ የማላንካራ ኦርቶዶክስ ሶርያ ቤተ ክርስቲያን ወይም የኦርቶዶክስ ሶርያዊ ምሥራቅ ቤተ ክርስቲያን ተብላ የምትጠራው የሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን፣ በሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ በ52 ዓ.ም. የተመሠረተች ጥንታዊት ናት፡፡ በደቡብ ሕንድ የምትገኘው ኬሬላ ወይም ማላንካራ፣ የክርስትናው መሠረት የተጣለባት የመንበሩ መቀመጫ ስትሆን፤ ካቶሊኮስ የሚለው የርእሰ መንበሩ ሥያሜም የፓትርያርክ አቻ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ በአሁኑ ወቅት ቤተ ክርስቲያኒቱ፣ በሊቃነ ጳጳሳት የሚመሩ 25 የሀገር ውስጥና የውጭ አህጉረ ስብከትን እንዳቋቋመችና ከ2.5 ሚሊዮን በላይ ተከታዮች እንዳሏት መረጃዎች ያሳያሉ፡፡
በሌላ በኩል፣ ትውልደ ሕንዳውያንና የኦርቶዶክስ ክርስትና ተከታይ የሆኑ በርካታ ተሳላሚዎች፣ የሕንዱን ፓትርያርክ በመከተል በአዲስ አበባ የመስቀል ዐደባባይ ተገኝተው የደመራን በዓል እንደሚያከብሩ ታውቋል። ነዋሪነታቸውን በሕንድ፣ በአሜሪካና በእስራኤል ያደረጉ መነኰሳትን፣ ካህናትንና ምእመናንን ያካተተውና በአርባ አምስት ቡድን የተደራጀው ይኸው የተሳላሚዎቹ መንፈሳዊ ጉዞ፣ በአንጋፋው የሙምባዩ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ የሚመራ እንደሆነ ተነግሯል፡፡ የጠቅላይ ጽ/ቤቱ ምንጮች እንደገለጹት፣ ተሳላሚዎቹ፣ “በኢትዮጵያ ገዳማት ሥርዓትና አኗኗር ዝና ተስበው የመጡ መንፈሳውያን ተጓዦች ናቸው፡፡” በኒውዴልሂ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቢሮ አስተባባሪነት በተዘጋጀው ጉብኝት ፓኬጅ መሠረትም፣ የደመራን በዓል በመስቀል ዐደባባይ ተገኝተው ያከብራሉ፤ የላሊበላ ደብር ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን፣ የጣና ገዳማትንና የጠቅላይ ጽ/ቤቱን ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር ይጎበኛሉ፤ ብለዋል - ምንጮቹ፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንድ እናት ቢምቢ ትንኝና ልጅ ቢንቢ ትንኝ ነበሩ፡፡ ልጅዬዋ ቢምቢ፤ በአገሩ እየተዘዋወረች ዙሪያ ገባው ውስጥ ነዋሪ - የሆኑትን እንስሳት፣ አዕዋፍና ነብሳት ልትጠይቃቸው ጎራ ልትል አሰበች፡፡ ይህንን ያወቀችው እናት፤
“መሄዱንስ ሂጂ፡፡ ዘመድ ማግኘትና መጠየቅ በጣም ጥሩ ነው፡፡ ነገር ግን ወዳጅና ጠላትሽን መለየት ይኖርብሻል፡፡ ጠላት የመሰለሽ ወዳጅ ሆኖ ይገኛል፡፡ ወዳጅ ያልሺው ደግሞ፣ ጠላት ሆኖ ተለውጦ ታገኚዋለሽ። ለማንኛውም ማጣራትን የመሰለ ነገር የለም፡፡”
ልጅዬዋ ቢምቢም፤
“እሺ እማማ፣ ቀስ ብዬ እያጣራሁ ለማየት እሞክራለሁ” ብላ አካባቢዋን ልታጠና መንገድ ቀጠለች፡፡
መጀመሪያ ቢራቢሮን አገኘች፡፡ “ቢራቢሮ እንደምነሽ?”
ቢራቢሮ፤
“ደህና ነኝ” አለች፡፡
“በአካባቢው ያሉ ነብሳት ተስማምተውሽ ይኖራሉ?”
“አዎን፡፡ ግን ክረምትም በጋም ሳልቸገር ለመኖር በመቻሌ፣ ወረተኛ ነሽ እያሉ ይወቅሱኛል”
“እነሱ ምን ፈልገው ነው?”
“ወይ የበጋ ሁኚ ወይ የክረምት ሁኚ ነው የሚሉኝ”
“ቆይ፤ ስለዚህ ጉዳይ እናቴን ጠይቄ ምን እንደምትል እነግርሻለሁ” ብላት ቢምቢ ሄደች፡፡
ቀጥላ ጦጣን አገኘቻት፡፡
“ጦጢት እንደምንድነሽ?”
“ደህና ነኝ”
“ከእንስሳቱ ጋር ስትኖሪ ምን ችግር ገጥሞሽ ያውቃል?”
“ምንም ችግር አልገጠመኝም፡፡ ግን ሁሉም በአንድነት በእኔ ላይ ፈርደው ብልጣ - ብልጥ ብትሆኚ ምን አለበት ታዲያ?”
“ታታልይኛለሽ፡፡ ታሞኚኛለሽ እያሉ ነው፡፡”
“የራሳቸው ጅልነት ነው ተያቸው” ብላ ቢምቢ መንገድ ትቀጥላለች፡፡
ብዙም ሳትሄድ አንበሳን አገኘችው፡፡
ቢምቢ፤
“ደህና ዋልክ አያ አንበሶ?”
“ደህና ነኝ፤ ቢምቢ”
“እንስሳት አብረውህ ሲኖሩ ምን ይሉሃል?”
“ጉልበተኛ ነህ፡፡ አምባገነን ነህ፤ ነው የሚሉኝ” አለ እየተጎማለለ፡፡
“አቅም ስላነሳቸው ነው እነሱ፡፡ ተዋቸው፡፡” ብላው መንገዷን ቀጠለች፡፡
በመጨረሻ የተሰበሰቡ ሰዎች አግኝታ፣ እነሱን አዳመጠችና፣ እየመሸ ስለመጣ ወደ እናቷ ተመለሰች፡፡
የሆነችውን ሁሉ ነገረቻት፡፡
“ሰዎችስ ምን አሉሽ?” አለቻት እናት ቢምቢ፡፡
ልጅየዋ ቢምቢም፤
“ይገርምሻል፤ ሰዎችማ ሲያጨበጭቡልኝ ዋሉ” አለቻት፡፡
እናት ቢምቢም፤
“ልጄ ሁለተኛ እንዳትሳሳቺ! እንደ፣ሰዎች ክፉ የለም፡፡ ያጨበጨቡልሽ የመሰለሽም በመዳፍና መዳፋቸው ጨፍልቀው ሊገድሉሽ ሲሞክሩ ነው፡፡ ስለዚህ ዳግመኛ እንዳትታለይላቸው!” አለችና መከረቻት፡- “ማጨብጨብ የሰው ልጆች ኃይለኛ መሳሪያ ነው፤ ተጠንቀቂ!”
*           *           *
አክራሪ መሆን መጥፎ የመሆኑን ያህል አድር - ባይና ወላዋይ መሆንም ያንኑ ያህል አስቸጋሪ ጠባይ ነው! ብልጣ ብልጥ መሆን የራሱ ችግር እንዳለው ሁሉ፣ ሞኛ - ሞኝ መሆንም ለማንም ብልጥ - ነኝ - ባይ የማታለል ተግባር ሰለባ ስለሚያደርግ፤ መጠንቀቅ ተገቢ ነው! አምባገነንነት ሁልጊዜ አያበላም፡፡ በእርግጥም የተገፉ፣ የተበደሉ፣ ፍትሕ - ያጡ፣ የተመረሩ ህዝቦች በተነሱ ጊዜ ማናቸውም ፈላጭ - ቆራጭ አገዛዝ አሳሩን ያያል፡፡ በዓለም ላይ ስንት አምባገነኖች ተሰባብረው እንደወደቁ ማሰላሰል ነው! የደገፉ መስለው ጧት ማታ ሲያጨበጭቡልን ጤነኛ መስለውን፤ “አሁን ነው ራስን ማሳየት” ብሎ ብቅ ማለት አደጋ አለው! ለመውረድ ብዙ ሽቅብ መውጣትም ክፉ ባህሪ ነው፡፡ ሁሉን፣ ሁልጊዜ አገኛለሁ ማለትም ግብዝነት ነው፡፡ እያጨበጨቡ ጎል ከሚከቱን ይሰውረን!
ዛሬ የትምህርት ጊዜ ነውና ትምህርታችንን ይግለጥልን፡፡ እንደ እስያ፤ “ዕውቀት እያለ የሚማር ጠፋብን” የሚል ትራጀዲ ውስጥ እንዳንገባ አምላክ ይጠብቀን!
“ምዕራቡ ዓለም ሲያስነጥስ ሌላው ክፍለ ዓለም ኒሞኒያ ይይዘዋል” የሚለውን በማሰብ፤ እንዳይምታታብን ራሳችንን እንቻል! የራስን የመሰለ ምንም ነገር የለም፡፡
የመጨረሻው እንግሊዛዊ የህንድ ገዢ ሎርድ ሉዊ፣ ለማህታማ ጋንዲ እንዲህ አለው “እኛ ከወጣን በህንድ አገር ቀውስ ይፈጠራል!”
ይሄኔ ማህታማ ጋንዲ፤
“አዎን ቀውስ ይፈጠራል - ቀውሱ ግን የራሳችን ነው!” አለና፤ ኩም አደረገው፡፡
“የራሳችንን ቀውስ ‘ራሳችን እንፈታዋለን!”
አንድ ፀሐፊ ካነበብናቸው በርካታ መጣጥፎች አንዱ ላይ፤ “የአዕምሯችን ማዕከል፣ እና ደጃፉም ሆነ ግንባሩ በጣም ሩቅ ለሩቅ ናቸው! ግን ተቀናጅተው ሥራ ይሰራሉ” ይላል፡፡ የእኛም ተግባር እንደዚሁ የተቀናጀ መሆን ይኖርበታል! ከተሳሰብንና ከተናበብን የስሌት ስህተት አንሰራም፡፡ የፍርድ ማዛባት ስህተት አንሰራም፡፡ የመረዳዳት ማቃት ስህተት አንሰራም፡፡
ዛሬ “ነፃ ኢኮኖሚ”፣ “ዲሞክራሲ”፣ “መልካም አስተዳደር” አስፈላጊ ነው ብለን ተፈጥመናል፡፡ ያም ሆኖ የፌደራሊዝምን ስርዓት፣ በተለይ የብሔር ብሔረሰብን ፌደራሊዝም ጨርሶ ካላደገው ካፒታሊዝማችን ጋር አብረን ለማስኬድ ብዙ እንቅፋት ሲፈጠርብን ይታያል፡፡ ኦሊቨር ጎልድስሚዝ የተባለው ገጣሚ፤ “ሀብት ይከማቻል ሰው ይበሰብሳል” ወደ ውስጥ እያየን፣ ራሳችንን እንፈትሽ፡፡ ነፃ ኢኮኖሚ ስንል በምን የዕድገት ደረጃ ላይ ላለ ኢኮኖሚ ነው ያጨነው? ብለን እንጠይቅ፡፡ ዲሞክራሲ ስንል በምን ደረጃ ላለ አገር ነው ያስቀደድነውና ስፌቱን የምንመርጠው? እንበል፡፡ ከፊውዶ ቡርዥዋ ሥርዓት ገና ሙሉ ለሙሉ ባልተላቀቀ ፖለቲካል-ኢኮኖሚ ላይ መልካም አስተዳደርን መጋለብ ቀርቶ መፈናጠጥስ ይቻላል ወይ? ብለን እንጠይቅ! ታላቅ ኃይል ያዘለውን ካፒታሊዝም፤ ከማህበረሰባዊ ኮንሰርቫቲዝም ጋር ማጋባትስ አማራጭ ይሆናል ወይ? (ምናልባት የቻይናን፣ የህንድን ስነልቦና ቢሰጠን) ብለን እንመርምር፡፡
የንድፈ-ሀሳብ መንገዳችን ከረኮንች ነው፡፡ እንኳንስ አስፋልት ኮብል-ስቶኑም ገና እያንገዳገደን ነው፡፡ ቆም ብሎ የሚያስብ አስተዋይ አዕምሮ አሁንም ያስፈልገናል! ከዕለታት አንድ ቀን የያዝነው ቲዎሪ ስህተት ሆኖ ቢሆንስ? ብለን መጠያየቅ አይከፋም፡፡ ለሁሉም ህመም አንድ መድኃኒት በመስጠት (ፓናሲያ እንዲሉ) ፈውስ እናገኛለን ብሎ ማሰብ ቀቢፀ- ተስፋ ነው፡፡ ማርክ ትዌይን፤ “መዶሻ ያለው ሰው፣ እያንዳንዱ ችግር ሚሥማር ይመስለዋል!” የሚለው በእኛ ዓይነቱ ላይ ሲሳለቅ ነው፡፡ ከዚህም ይሰውረን፡፡
ለክርስትና ዕምነት ተከታዮች መልካም የመስቀል በዓል!  

      ሚዩዚክ ሜይዴይ ከኢትዮጵስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር፣ ነገ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ በብሄራዊ ቤተ መፃህፍትና ቤተመዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ፣ በአለቃ ዘነበ እና በአለቃ ወልደማሪያም በተፃፉ የአፄ ቴዎድሮስ ዜና መዋዕሎች ላይ ውይይት ያካሂዳል፡፡ ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት ገጣሚና ደራሲ ይታገሱ ጌትነት ሲሆን በዝግጅቱ ላይ ለመሳተፍ ፍላጎት ያለው ሁሉ እንዲሳተፍ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ጋብዟል፡፡

ባለፈው ሰኞ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት አዲስ ማዕቀብ የተጣለባት ሰሜን ኮርያ፣ ይህ ማዕቀብ እንዲጣልብኝ ቁልፍ ሚና ተጫውተዋልና እቀጣቸዋለሁ በሚል፣ “ጃፓንን በውሃ ማዕበል አሰምጣለሁ፣ አሜሪካን ደግሞ ዶግ አመድ አደርጋለሁ” ስትል መዛቷን ዘ ጋርዲያን ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት፣ በቅርቡ ካደረገቺው የኒውክሌር ሙከራ ጋር በተያያዘ በሰሜን ኮርያ ላይ ባለፈው ሰኞ አዲስ ማዕቀብ መጣሉን ያስታወሰው ዘገባው፤ የአገሪቱ መንግስት የውጭ ግንኙነት ኮሚሽንም ይህን አድርጋለች በሚል በአሜሪካ ላይ ከተለመደው በተለየ መልኩ ጠንከር ያለና ብዙዎችን ያነጋገረ ዛቻ መሰንዘሩን ገልጧል፡፡
የሰሜን ኮርያ መንግስት የዜና ወኪል ሃሙስ ዕለት ባሰራጨው ዘገባ፤ የሰሜን ኮርያ መንግስት አራት የጃፓን ደሴቶችን በኒውክሌር ቦንብ ጥቃት ውሃ ውስጥ እንደሚያሰምጥና አሜሪካንም በከፍተኛ ጥቃት ዶግ አመድ እንደሚያደርግ አስታውቋል፡፡
ይህን ተከትሎ የጃፓን መንግስት ቃል አቀባይ፣ የሰሜን ኮርያን ዛቻ “ጸብ አጫሪና እጅግ አደገኛ” በሚል ማውገዛቸውንና ዛቻው በአካባቢው ያለውን ውጥረት የሚያባብስና ተቀባይነት የሌለው ነው በሚል ማጣጣላቸውንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡
ዘ ኢንዲፔንደንት በበኩሉ፣ 15 አባላት ያሉት የተመድ የጸጥታው ምክር ቤት፣ ሰሜን ኮርያ የጨርቃ ጨርቅ ምርቶችን ወደ ውጭ አገራት እንዳትልክ የሚከለክለውንና በአሜሪካ የረቀቀውን የማዕቀብ ሃሳብ ባለፈው ሰኞ ማጽደቁ በአካባቢው ያለውን ውጥረት የበለጠ እንዳባባሰው ዘግቧል፡