Administrator

Administrator

 ጎግል የ5 ቢሊዮን ዶላር ቅጣት ተጣለበት


    ታዋቂው የማህበራዊ ድረገጽ ትዊተር በግንቦትና በሰኔ ወር ብቻ ህገወጥ ድርጊት የሚፈጽሙና የተጭበረበሩ ያላቸውን የ70 ሚሊዮን ያህል ተጠቃሚዎቹን አካውንቶች በመዝጋት አገልግሎቱን እንዳያገኙ ማድረጉን ዋሽንግተን ፖስት ዘግቧል፡፡
የተጭበረበሩና ህገወጥ ድርጊቶችን በሚፈጽሙ ተጠቃሚዎቹ ላይ የሚያደርገውን ቁጥጥርና የሚወስዳቸውን እርምጃዎች እያጠናከረ የመጣው ትዊተር፤ የተጠቃሚዎቹን ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ የመቀነስ እርምጃው ገቢውንና ትርፋማነቱን አደጋ ውስጥ እንዳይከተው መሰጋቱን ዘገባው አመልክቷል፡፡
እ.ኤ.አ በ2016 ከተካሄደው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ቅስቀሳ ጋር በተያያዘ ተጠቃሚዎች ያልተገባ ድርጊት መፈጸማቸውን ተከትሎ  የተጭበረበሩ አካውንቶችን በመጠቀም የተሳሳቱ መረጃዎችንና አደገኛ መልዕክቶችን በሚያሰራጩ ተጠቃሚዎች ላይ የሚወስደውን እርምጃ ያጠበቀው ትዊተር፤ ባለፈው የፈረንጆች አመት 2017 የመጨረሻዎቹ አራት ወራት ጊዜ ውስጥ ብቻ የ58 ሚሊዮን ተጠቃሚዎቹን አካውንቶች መዝጋቱን የዘገበው ደግሞ አሶሼትድ ፕሬስ ነው፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ የአውሮፓ ህብረት የንግድ ውድድርንና የሞባይል ተጠቃሚ ደንበኞችን ምርጫ የሚገድብ ህገወጥ ድርጊት ፈጽሟል በሚል ባለፈው ረቡዕ በታዋቂው የአሜሪካ ኩባንያ ጎግል ላይ ክብረወሰን የተመዘገበበትን የ5 ቢሊዮን ዶላር ቅጣት ማስተላለፉ ተዘግቧል፡፡
ጎግል የራሱ ምርት የሆነውን አንድሮይድ ኦፐሬቲንግ ሲስተም የሚጠቀሙ የሞባይል ስልኮችን የሚያመርቱ ኩባንያዎችን፣ የራሱ ምርት የሆኑ ሌሎች የፍለጋ አፕሊኬሽኖችን ኢንስቶል እንዲያደርጉ አስገድዷል በሚል ከአውሮፓ ህብረት የተላለፈበትን የገንዘብ ቅጣት ውሳኔ እንደማይቀበልና ይግባኝ እንደሚጠይቅ አስታውሷል፡፡
የአውሮፓ ህብረት ከሶስት አመታት ምርመራ በኋላ በጎግል ላይ ያስተላለፈው ይህ የገንዘብ ቅጣት፣ በታሪኩ ከንግድ ውድድር ህጎች ጥሰት ጋር በተያያዘ በአንድ ኩባንያ ላይ የጣለው ከፍተኛው ገንዘብ እንደሆነም አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡

 በ50 የተለያዩ የዓለማችን አገራት የኤችአይቪ ኤድስ ስርጭት እየጨመረ መምጣቱንና በቫይረሱ እየተጠቁ ካሉት ሰዎች ግማሽ ያህሉ የመድሃኒትና የህክምና አገልግሎቶችን እያገኙ እንዳልሆነ ዩኤንኤድስ የተባለው አለማቀፍ ተቋም ባወጣው ሪፖርት አስታውቋል፡፡
የኤችአይቪ ቫይረስን ስርጭት ለመግታት በአለማቀፍ ደረጃ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት እየተዳከሙ መሆናቸውን የጠቆመው የተቋሙ ሪፖርት፤ በ50 ያህል የአለማችን አገራት የቫይረሱ ስርጭት ጭማሪ ማሳየቱም ለጉዳዩ የሚሰጠው ትኩረት አናሳ እየሆነ መምጣቱን እንደሚያመላክት ገልጧል፡፡
የቫይረሱ ስርጭት በአንዳንድ አገራት ጥሩ በሚባል ሁኔታ መቀነስ ማሳየቱን የጠቆመው ዘገባው፤ በአለማችን በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ የቀነሰው ከዚህ በፊት በቫይረሱ ክፉኛ በተጠቁት የምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ አገራት ሲሆን፣ ለዚህ መሻሻል በምክንያትነት የጠቀሰውም የህብረተሰቡ ግንዛቤ በጥሩ ሁኔታ ማደጉና አብዛኞቹ የቫይረሱ ተጠቂዎች የኤችአይቪ ህክምና በአግባቡ ማግኘታቸው መሆኑን አስረድቷል፡፡
በምዕራብና በመካከላዊ አፍሪካ አገራት የኤችአይቪ ህክምና አገልግሎት ማግኘት የሚገባቸው በርካታ ዜጎች የአገልግሎቶች ተጠቃሚ አይደሉም ያለው ሪፖርቱ፤ በአገራቱ 75 በመቶ ህጻናት እና 60 በመቶ አዋቂዎች የሚገባቸውን የኤችአይቪ ህክምና እንዳላገኙም ጠቁሟል፡፡   
በአሁኑ ወቅት በመላው አለም በኤችአይቪ ቫይረስ የተጠቁ 37 ሚሊዮን ያህል ሰዎች መኖራቸውን የዘገበው ቢቢሲ በበኩሉ፣ በአለማችን የተለያዩ አገራት በየአመቱ አንድ ሚሊዮን ያህል ሰዎች በቫይረሱ ሳቢያ ለህልፈተ ህይወት እንደሚዳረጉም አመልክቷል፡፡

 - 9 ሚሊዮን አፍሪካውያን በከፋ ባርነት ውስጥ ይኖራሉ
  - በአለማችን ባለፉት 19 ወራት 40ሚ. ሰዎች የባርነት ሰለባ ሆነዋል

    ሰሜን ኮርያና ኤርትራ በርካታ ዜጎች ለዘመናዊ ባርነት ተዳርገው የሚኖሩባቸው ቀዳሚዎቹ የአለማችን አገራት መሆናቸውንና ባለፉት 2 አመታት በመላው አለም ከ40 ሚሊዮን በላይ የተለያዩ አገራት ዜጎች የዘመናዊ ባርነት ሰለባዎች መሆናቸውን ዎክ ፍሪ ፋውንዴሽን የተባለው አለማቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ተቋም አስታውቋል፡፡
ተቋሙ ከትናንት በስቲያ ይፋ ባደረገው የ2018 የፈረንጆች አመት አለማቀፍ የባርነት ደረጃ ሁኔታ አመላካች ሪፖርት፣ ሰሜን ኮርያ በቀዳሚነት የተቀመጠች ሲሆን ከአገሪቱ አጠቃላይ ህዝብ 10 በመቶ የሚሆነው የዘመናዊ ባርነት ሰለባ መሆኑን አስታውቋል፡፡ በአመቱ የተቋሙ ሪፖርት ከአለማችን አገራት ሁለተኛ ደረጃን በያዘቺው ኤርትራም፣ በርካታ ቁጥር ያላቸው ዜጎች በብሔራዊ ውትድርና ግዳጅና በሌሎች የጉልበት ብዝበዛዎች ለአስርት አመታት የከፋ የባርነት ኑሮን ሲገፉ ኖረዋል መባሉን የዘገበው ሮይተርስ፤ በሪፖርቱ ሶስተኛ ደረጃን የያዘቺው ብሩንዲ መሆኗንም ጠቁሟል፡፡
በሶስቱም አገራት መንግስታት ዜጎቻቸውን ለጉልበት ብዝበዛና ለሌሎች የዘመናዊ ባርነት ጭቆናዎችና ድርጊቶች እየዳረጉ እንደሚገኙ የጠቆመው የሮይተርስ ዘገባ፤ በመላው አፍሪካ ከ9 ሚሊዮን በላይ አፍሪካውያን አስከፊ የባርነት ኑሮን በመግፋት ላይ እንደሚገኙም በሪፖርቱ መጠቀሱንም አመልክቷል፡፡
በተለያዩ አለማችን አገራት የሚከሰቱ ግጭቶችና የአገራት መንግስታት የሚያሳድሩት ጭቆና በርካታ ቁጥር ያላቸውን ዜጎች ለከፋ ዘመናዊ ባርነት መዳረጋቸውን የጠቆመው ሪፖርቱ፤ ዘመናዊ ባርነት ተስፋፍቶባቸዋል በሚል ከጠቀሳቸው ሌሎች አገራትም ውስጥ መካከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ አፍጋኒስታን፣ ደቡብ ሱዳንና ፓኪስታን ይገኙበታል፡፡
እ.ኤ.አ ከ2016 አንስቶ ባለው ጊዜ ውስጥ በመላው አለም ከ40 ሚሊዮን በላይ የተለያዩ አገራት ዜጎች የዘመናዊ ባርነት ሰለባዎች ሆነዋል ሲሉ ዎክ ፍሪ ፋውንዴሽንና አለማቀፉ የስራ ድርጅት ማስታወቃቸውን የዘገበው ሮይተርስ፤ ተቋሙ እ.ኤ.አ በ2016 ይፋ ባደረገው ሪፖርቱ ከአለማችን አገራት መካከል በርካታ ቁጥር ያላቸው ዜጎች የዘመናዊ ባርነት ሰለባዎች የሆኑባት ቀዳሚዋ አገር ህንድ እንደነበረችና በአመቱ 18.4 ሚሊዮን ያህል ህንዳውያን የዘመናዊ ባርነት ሰለቦች እንደነበሩም አስታውሷል፡፡

  የጸረ-አፓርታይድ ታጋዩና የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት ኔልሰን ማንዴላ 100ኛ ዓመት የልደት በአል ባለፈው ረቡዕ በደቡብ አፍሪካና በሌሎች አገራት በተለያዩ ዝግጅቶች መከበሩን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ደቡብ አፍሪካውያን ከአምስት አመታት በፊት ከዚህ አለም በሞት የተለዩትን ኔልሰን ማንዴላን መልካም ስራዎችና አፓርታይድን በመታገል ያበረከቱትን ታሪካዊ አስተዋጽኦ በመዘከርና የበጎ አድራጎት ስራዎችን በማከናወን የ100ኛ ዓመት የልደት በአላቸውን ማክበራቸው ተነግሯል፡፡
ያም ሆኖ ግን፣ ጥቂት ደቡብ አፍሪካውያን ማንዴላ የታገሉለት የቀለም ልዩነትና ኢ-ፍትሃዊ የሆነ የሃብት ክፍፍል ለዘመናት ተሻግሮ አሁንም ድረስ ስር ሰድዷል በሚል የማንዴላን ስኬት ጥያቄ ውስጥ መክተታቸውንና የልደት በአሉ በመከበሩ ደስተኞች አለመሆናቸውን ሲገልጹ መደመጣቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡
የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፤የማንዴላን የልደት በዓል ምክንያት በማድረግ ከ44 የተለያዩ አገራት ለተውጣጡና በኦባማ ፋውንዴሽን የአፍሪካ ሊደርሺፕ ፕሮግራም ለታቀፉ 200 ወጣት አፍሪካውያን መሪዎች በጆሃንስበርግ አነቃቂና የማንዴላን ታላቅነት የሚዘክር ንግግር ማድረጋቸውንም ዘገባው አመልክቷል፡፡


              ከአዲስ አበባ ከ800 በላይ ሰው ይጓዛል
            በጉራጌ ልማትና ባህል ማህበር አስተባባሪነት ዛሬ ለስድስተኛ ጊዜ በሚካሄደው የችግኝ ተከላ ዘመቻ፣ በጉራጌ ዞን በ13ቱም ወረዳዎች ከ8 ሚ. በላይ ችግኞች እንደሚተከሉ የጉራጌ ልማትና ባህል ማህበር አስታወቀ፡፡ በችግኝ ተከላው ከ1 ሺህ ሰዎች በላይ የሚሳተፉ ሲሆን ከአዲስ አበባ ብቻ ከ800 በላይ ሰው ወደ ስፍራው እንደሚያቀና የማህበሩ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ መንግስቱ ኃይለማሪያም ተናግረዋል፡፡
ማኅበሩ ላለፉት አምስት ዓመታት ያለማቋረጥ በጉራጌ ዞን ወረዳዎች በርካታ ችግኞችን ከመትከሉም በላይ መፅደቃቸውን በማረጋገጥና በመንከባከብ በኩልም ውጤታማ ስራ መሥራቱን ኃላፊው ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ በማህበሩ ጽ/ቤት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቀው፣ ለችግኝ ተከላው የሚያስፈልገውን ከአንድ ሚ. ብር በላይ ከአካባቢው ተወላጅ ባለሀብቶችና ከተለያዩ ድርጅቶች መሰብሰብ መቻሉን ገልፀዋል፡፡
ከአዲስ አበባ ሚኒስትሮች፣ ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ የተለያዩ ቢሮ ኃላፊዎች፣ የፓርላማ አባላት፣ ባለሀብቶች፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኃላፊዎች ከክፍለ ከተሞችና ከወረዳዎች፣ እንዲሁም የተለያዩ የህብረተሰብ ተወካዮችና ታዋቂ ግለሰቦች በዛሬው የችግኝ ተከላ ላይ ይሳተፋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅና ለጉዞውም ከ14 በላይ አውቶብሶች መዘጋጀታቸውን አቶ መንግስቱ ኃ/ማርያም ጨምረው ገልፀዋል፡፡
የጉራጌ ልማትና ባህል ማዕከል፤ በጤና፣ በትምህርት በባህል ማበልፀግና በተለያዩ ዘርፎች የልማት ስራዎችን በመስራት የሚታወቅ ሲሆን በተጨማሪም ከደን ምንጣሮና ከአካባቢ መራቆት፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ የመጣውን የአየር ንብረት ለውጥ ለመቋቋምና አካባቢውን ጤናማ ለማድረግ ወደ ችግኝ ተከላ ፊቱን በማዞር፣ ውጤታማ ስራ መስራት መቻሉንና ይሄው ተግባር በየዓመቱ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ኃላፊው አስታውቀዋል፡፡

Saturday, 21 July 2018 13:05

ወንዶችና የጡት ካንሰር…

  ….አንድ ስራ ልቀጠር አስቤ በቅድሚያ የጤና ምርመራ ማቅረብ ስለነበረብኝ ወደ ሕክምና ባለሙያ ዘንድ ቀረብኩ። እሱም …የሚሻለው ወደ ግል ሐኪምህ ሄደህ ብትታይ ጥሩ ነው …አለኝ፡፡ ወደሁዋላ መለስ ብዬ ሳስበው…ላለፉት ሁለት አመታት አንድ ችግር ገጥሞኝ ነበር፡፡ በሰውነቴ ላይ በተለይም በጡቴ አካባቢ አንድ ትክክል ያልሆነ ተፈጥሮአዊ ቅርጽ ማየት ጀመርኩ፡፡ ለካስ የጡት ካንሰር የሚባል በሽታ ቀስ በቀስ እየተስፋፋ ኖሮአል፡፡ እኔ የነበረኝን ስሜት ችላ ብዬ ነበር የቆየሁት። አሁን ግን ሕይወቴ አደጋ ላይ ነው፡፡
አንድ ምክር አለኝ፡፡ እባካችሁ ማንኛችሁም ብትሆኑ ትንሽ ነገር ነው ብላችሁ ችላ አትበሉ፡፡ ምንም አዲስ ነገር ቢሰማችሁ በፍጥነት ወደባለሙያዎች በመቅረብ ምንነቱን ተረዱ፡፡
ጽሁፉን ያገኘንበት ምንጭ ያሰፈረው የግለሰብ ታሪክ ነው፡፡
የጡትን ተፈጥሮ ስንመለከት ወንዶችም ሴቶችም ከተፈጥሮ የሰውነት አካላቸው መካከል ጡት የሚባል ነገር መኖሩ እሙን ነው፡፡ የሴቶች ጡት በተፈጥሮአቸው ባላቸው ሆርሞን ሳቢያ እንዲያድግና የተለያዩ ተፈጥሮአዊ ግዴታዎችን እንዲወጣ የሚያስችል ይሆናል፡፡ የወንዶች ጡት ግን በደረት ላይ ተፈጥሮውን ለማመላከት ያህል ይታያል እንጂ ወደየትም የማያድግ እና ምንም የተለየ አገልግሎት ማለትም ለልጆች እንደወተት መስጠት የመሳሰሉትን ግዴታዎች እንዲወጣ የማይጠበቅ ነው። በእርግጥ ሴቶች ጡታቸው ወተት የሚያመርተው ከእርግዝና ጋር በተያያዘ በሚኖር ተፈጥሮአዊ ሂደት ነው፡፡
የጡት ካንሰር ለወንዶች አልፎ አልፎ የሚከሰት ሕመም እንጂ እንደሴቶቹ በስፋት የሚስ ተዋል አይደለም። ምናልባትም ከሚከሰቱት የጡት ካንሰር ሕመሞች ከ1% በታች የሚሆነው በወንዶች ላይ የሚከሰት ይሆናል፡፡ ወንዶች በሕይወት ዘመናቸው በጡት ካንሰር ሕመም የሚ ጠቁት ከ1000/ከአንድ ሺህዎቹ አንድ ሰው ቢሆን ነው፡፡ ይሄ ሲታይ ምናልባትም ወንዶች የጡት ካንሰር ሕመም አይይዛቸውም ለማለት ሊያስደፍር ይችል ይሆናል፡፡ ነገር ግን እውነታው በመጠኑም ቢሆን ወንዶች ጡታቸውን ሊታመሙ ይችላሉ፡፡
ወንዶች የጡት ካንሰር ይዞአቸዋል የሚያሰኙ አንዳንድ ምልክቶች አሉ፡፡
በጡት ላይ የመጠጠር ወይንም የማበጥ ምልክት ይታያል፡፡ በእርግጥ ካልነኩት በስተቀር ሕመም ላይሰማ ይችላል፡፡
የጡት መደደር መኖሩ የማይታወቅ እና በራሱ ጊዜ በጡት ውስጥ ወዲያ ወዲህ የማይንቀሳቀስ ነው፡፡
የጡት ጫፍ አቅጣጫ ጠመም የማለት ነገር ሊታይበት ይችላል፡፡
ከጡት ጫፍ ፈሳሽ የመውጣት ነገር ይስተዋላል፡፡አንዳዴም የደም ምልክት ሊታይበት ይችላል፡፡
በጡት ጫፍ ዙሪያ ምቾት የማይሰጥ የህመም ስሜት ሊኖር ይችላል፡፡
የጡት ጫፍ ወይም በዚያ አካባቢ ባለው ቆዳ ላይ የመቅላት የመደደር ወይንም የማበጥ ሁኔታ ይስተዋላል፡፡
ወንዶች ብዙ ጊዜ ይህ ህመም ይደርስብኛል ብሎ ካለማሰብ ነገሩን ችላ የማለት ነገር ይስተዋ ልባቸዋል። በእርግጥ ሁኔታው እንደሴቶቹ በተስፋፋ መልኩ የሚያጋጥም ባይሆንም እንደችግር ግን መስተዋሉ አይቀርም፡፡  
ለጡት ካንሰር ወንዶች ሊጋለጡ የሚችሉባቸው የተለያዩ ምክንያቶች አሉ፡፡
እድሜ፤ ይህ በምክንያትነት ከሚጠቀሱት ውስጥ ከፍተኛውን ድርሻ የሚይዘው ነው፡፡ ልክ ሴቶች   በእድሜ ምክንያት ለጡት ካንሰር እንደሚጋለጡት ሁሉ ወንዶችም ይጋለጣሉ። ወንዶች በእድ ሜያቸው ወደ 68/አመት ሲሆናቸው ለጡት ካንሰር የመጋለጥ እድል ሊያጋጥማቸው ይችላል፡፡ ከፍተኛ የኢስትሮጂን መጠን፤ በጡት አካባቢ ያሉ ሴሎች እድገት በትክክለኛውም ወይንም ትክክል ባልሆነው መንገድ የሚከሰት ሲሆን ኢስትሮጂን እንዲኖር ያደርጋል፡፡ ወንዶች በከፍተኛ ደረጃ ይህ ኢስትሮጂን ሊያጋጥማቸው የሚችለው፤ የሆርሞን መድሀኒቶችን ከመውሰድ፤ ከልክ ያለፈ ክብደት ሲኖር፤ እና የኢስትሮጂን መመረትን የሚጨምር ሲሆን ነው፡፡
በአኑዋኑዋር ምክንያት ለኢስትሮጂን መጋለጥ ፤ የአልኮሆል መጠጦች ሱሰኛ መሆን፤ እና በዚህም የተነሳ ጉበት በደም ውስጥ ሊኖር የሚገባውን ኢስትሮጂን መመጠን ሲያቅተው፤ የጉበት በሽታ ሲኖር እና በዚህም ሳቢያ አንድሮጂን(የወን ዶችን ሆርሞን) ዝቅ ሲያደርገው እንዲሁም ኢስትሮጂንን ማለትም (የሴቶችን ሆርሞን )ከፍ ሲያደርገው ችግሩ ሊከሰት ይችላል፡፡:
ከቤተሰብ ጋር በተያያዘ ፤ ይህ የጡት ካንሰር ሕመም የነበረና ያለ ሲሆን በዘር ሊተላለፍ ይችላል፡፡
ለጨረር የመጋለጥ ሁኔታ ፤አንድ ወንድ በደረቱ አካባቢ በጨረር ሕክምና ከተረዳ ምናልባትም በዚያ ሳቢያ የጡት ካንሰር ሊይዘው ይችላል፡፡  
ከላይ የተጠቀሱትና ሌሎችም ለጡት ካንሰር ለመጋለጥ በተለይም ለወንዶች ምክንያት ይሆናሉ ተብለው ተጠቅሰዋል፡፡ የጡት ካንሰር ከምን ደረጃ ላይ ይገኛል የሚለውን ለመለየት የህክምና ባለሙያዎች እንደሚከተለው አስቀምጠዋቸዋል፡፡
ደረጃ 0፤ የጡት ካንሰሩ ምርመራ ሲደረግ በ0/ደረጃ ላይ ያለ ከሆነ የካንሰር ሴሉ ወደሌላ ሰውነት ሊሰራጭ ከማይችልበት ደረጃ ላይ ይገኛል ማለት ነው፡፡
ደረጃ 1፤ በደረጃ አንድ ላይ የሚገኝ የካንሰር ሴል በጊዜው የህክምና እርዳታ ካልተደረገለት ወደሌላ ሰውነት ሊሰራጭ እንደሚችል አመላካች ነው፡፡
ደረጃ 2፤ የካንሰር ሴሉ በደረጃ ሁለት ላይ ከተገኝ ትናንሽ የካንሰር ሴሎች በቡድን ወደአጎራባች የሰውነት ክፍሎች የተሰራጨ መሆኑን እና በእርግጥ ወደ ቲዩመር/ወይንም ወደዋናው የካንሰር መገለጫ እንዳላደጉ ወይም ደግሞ ከ2/ሴንቲ ሜትር በላይ ያላደገ ቲዩመር መኖሩን ይናገራል፡፡ በዚሁ በደረጃ ሁለት ቀጣዩ ነገር ወደሌሎች የሰውነት ክፍሎች ሊሰራጭ የሚችል የካንሰር ሴል መኖሩን እና እርዝመቱም ከ2-5 ሴንቲሜትር የሚገመት መሆኑን እንዲሁም ወደሌላ የሰውነት ክፍል መተላለፍ አለመተላለፉን በሚመለከት እርግጠኛውን ለመናገር የማያ ስችል ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ እስከ 2/ሴንቲሜትር የሚደርስ ቲዩመር ወደሌላ የሰውነት ክፍል ተላልፎ ሊገኝ ይችላል፡፡ የካንሰሩ ደረጃ በዚህ መልክ እድገቱን እየጨመረ የመስፋፋት አቅሙ ንም እያጠናከረ እስከ 5/አምስተኛ ደረጃ ድረስ ይቀጥላል፡፡ በደረጃ አራት ላይ የሚታየው  የጡት ካንሰሩ ወደሌላ የሰውነት ክፍል ተሰራጭቶ  ለከፍተኛ ሕመም የሚዳርግበትና በሕክምናም ለማዳን አስቸጋሪ የሚሆንበት ደረጃ ሲሆን ደረጃ 5/አምስት ደግሞ የመጨረሻው ክፍል ነው፡፡
        ምንጭ፡- Breast Cancer.com
የጡት ካንሰር መከላከያ ዋና መፍትሄ የሚባለው የህክምና ክትትል ማድረግ ነው ያሉን ዶ/ር መብራቱ ጀምበር የጽንስና ማህጸን ሕክምና ባለሙያ ናቸው፡፡ ዶ/ር ከዚህም በተጨማሪ የገለጹት እራስን መመርመር እንዴት ይቻላል የሚለውን ነው፡፡ ካንሰሩ መኖር አለመኖሩን ለመለየት ራስን በራስ መመርመር  ጠቃሚ ነው፡፡ ሰውነትን ሙሉ በሙሉ ወይም ግማሽ አካልን በሚያሳይ መስታወት ፊት ለፊት ቆሞ ሁለት እጅን ከሁዋላ ማጅራት ላይ በማስቀመጥ ጡት ወደፊት እንዲፈጥ በማድረግ የጡት ቆዳ ለስለስ ያለ ወይንም የተጨማደደ ነገር እንዳለበትና እንደሌለበት ማየት አንዱ ዘዴ ነው፡፡ ጡት በተፈጥሮው አፍንጫው አካባቢ ጠቆር ያለ ነው። ከተለመደው ውጪ የተለየ ጥቁረት ወይም የነጣ የገረጣ ለማሳከክም የሚጋብዝ ነገር ካለ ቶሎ  ማየት ያስፈልጋል። እንደገናም ጡትን በሃሳብ አራት ቦታ በመክፈል አራቱን ቦታዎች በጣት በመዳሰስ እጢ ወይም እብጠት.. የጓጐለ ነገር መኖር አለመኖሩን ማረጋገጥ ይገባል፡፡ ሌላው እራስን የመመርመሪያ ዘዴ ደግሞ ገላን በሚታጠቡበት ጊዜ ገላን ሳሙና ከቀቡ በሁዋላ ሲዳሰስ በበለጠ ተፈጥሮአዊ ያልሆኑ ነገሮችን ለማግኘት ያስችላል ፡፡ የጡትን አካባቢ ብቻ ፈትሾ ማቆም ደግሞ በቂ አይደለም ፡፡ወደብብትም ገብቶ በመዳሰስ እብጠት መኖር አለመኖሩን ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡

  ከዕለታት አንድ ቀን፤
አያ አንበሶ ለዱር እንስሳት ሁሉ አንድ መልዕክት አስተላለፈ፡-
“እስከ ዛሬ መኖሪያ ደናችን ላይ ጥፋት ያላደረሰ እንስሳ፣ እኔ ቤት መጥቶ ፀበል ይቅመስ!” አለ፡፡
የዱር እንስሳት ሁሉ እየተጋፉ መጡ፡፡ እራሳቸውን የተጠራጠሩ ግን ቀርተዋል፡፡
“አሁንስ አያ አንበሶ አበዛው! እንዳለፈው ጊዜ ቤቱ አስገብቶ ያለ የሌለ ሥራ ሊያሰራን ይሆናልኮ!” ብለው ጉልበታቸውን የሰሰቱና መልፋት አንፈልግም ያሉ ተሰወሩ፡፡
“ከዚህ ቀደም አያ አንበሶ በደል አድርሶብናል - የአስተዳደር ግፍ ፈፅሞብናል” ያሉና ያቄሙ ደግሞ አድራሻቸውን አጥፍተው ተቀመጡ፡፡
አያ አንበሶ ግን በየሰበብ አስባቡ ከድግሱ የቀሩትን ከምንም ሳይቆጥር፤ ከመጡት ጋር ያለውን ምግብ ለመቋደስ ተዘጋጀና ተበላ፣ ተጠጣ፡፡
በመጨረሻ ላይ፤
“ጎበዝ፤ እንግዲህ የሥራ ዘመን ነውና ቀበቶን ጠበቅ ማድረግ ያስፈልጋል! እስቲ ለመጪው ጊዜ ምን ማድረግ እንዳለብን ሀሳብ አምጡ” አለ፡፡
ጦጢት፤
“አያ አንበሶ፤ የተሰባሰብነው እንስሳት አንድ ዓይነት አይደለንም፡፡ አንዳንዶቹ ጨርሰው ከዚህ ቀደም መጥተው የማያውቁ ናቸው! መጥተው የነበሩና አሁን ግን በስንት ጊዜያቸው የመጡ አሉ፡፡ በረባ ባልረባው ከእኔና ከእርሶ ጋር ተቀያይመው ቀርተው የነበሩ አሁን ሀሳባቸውን ቀይረው ድግስ ለመብላት የመጡ አሉ፡፡ ድግሱን ሳይፈልጉት አያ አንበሶን ፈርተው የመጡም ይታያሉ፡፡ ከአያ አንበሶ ጋር አዲስ ፍቅር ያመናቅር ዓይነት ሆነው የመጡ አዲስ ግልብጦችም አሉ፡፡ ድንገት ደራሾች ናቸው፡፡ ብዙ ይበሉ ይጠጡ ይሆናል እንጂ ደህና ሀሳብ አያመጡም፡፡ እንዴት ብለን ተስማምተን አንድ የጋራ ሀሳብ እናመጣለን?” ብላ ተቀመጠች፡፡
“አጨብጭቤም ቢሆን እመለሳለሁ፣ ከድግስ አልቀርም ብሎ የመጣ አለ!” አለ አያ ዝንጀሮ፡፡
አያ ዝሆንም፤
“ሁልጊዜ በሞቀበት የሚዘፍንም ፀበል ሊቀምስ የመጣ አለ፡፡ በቀላሉ አንግባባም!” አለ፡፡
ሁሉም ተራ በተራ እንዲህ ያለ ሀሳብ ሰጡ፡፡ ውጤቱ የማይታወቅ ሁሉም እንስሳ የሚናገርበት ስብሰባ እየሆነ መጣ። የሚዘባርቀው፣ ሙግት የሚወደው፣ አንደበት አለኝ ከኔ በላይ ተናጋሪ ላሳር የሚለው … ሁሉም ልፍለፋ ቀጠለ፡፡ የጨረባ ተዝካር መሰለ፡፡
ጥቂት ቆይቶ ወደ ጠብ አመራ! ዝም በሉ ቢባል ማን ሊሰማ? “ሀሳብ ሥጡኮ ነው ያልኩት” ቢል አያ አንበሶ፣ ማን አደብ ሊገዛ? ሁሉም የኔን ሀሳብ የሚያክል የለም እያለ ጭራሽ ይዋጣልን እስከ መባባል ደረሰ!
ይሄኔ አያ አንበሶ ትዕግሥቱ አለቀ፡፡
“እንግዲህ ሁልሺም አርፈሽ ተቀመጪ፡፡ ትዕግስት ፍርሃት አይደለም፡፡ አዳሜ ትምህርት እንዲሆንሽ፣ ብጥበጣውን በጣም ያበዛውን አያ ነብሮን ምን እንደማደርገው ተመልከቺ” ብሎ ነብሮ ሳያስበው ክፉኛ ደቆሰው፡፡ ነብሮ ተብረክርኮ ወደቀ!
ይሄኔ ጦጢት፤
“ትላንትና ሞቼ በቀረሁ ሳልቀበር
 እኔም የፈራሁት ይሄንኑ ነበር” አለችና “አያ አንበሶ፤ ከእንግዲህ እርሶ ባሉት እስማማለሁ!” ብላ ውልቅ አለች፡፡
ሁሉም “ዓመት ዓመት ያድርሰን! የዓመት እንስሳ ይበለን!”
እያሉ ጦጢት በቀደደችው ወጡ፡፡ አንዳንዶቹ ግን “እሱ ነው! እሱ ነው!” እያሉ ለአያ አንበሶ፤ በጥባጩን እየወነጀሉ፣ አስመዝግበው ተመስግነው ወጡ፡፡
አያ አንበሶም፤ “ለአህያ ማር አይጥማት”፤ ያሉት አባቶቻችን ዕውነታቸውን ነው!” ብሎ አሰናበታቸውና “በሚቀጥለው ዓመት አሳያቸዋለሁ!” አለ በሆዱ፡፡
*   *   *
አለመግባባት ክፉ አባዜያችን ነው! ዘይትና ውሃ አይቀላቀሉም፡፡ ብዙዎች የሚመሳሰሉ ይመስላቸዋል እንጂ ፈታኝ ወቅት ሲመጣ ሀሳባቸውም ይበታተናል፡፡ ዋንኛው ችግር በአካልም በሥነ ልቦናም አለመዘጋጀት ነው፡፡ ለመዘጋጀት የጊዜ ዕቅድ ያስፈልጋል፡፡ በጊዜ፣ በተገቢ ጉዳይ ላይ አስቦ፣ ወጥኖ መነሳትን ይጠይቃል፡፡ ድንገት ተሰብስቦ፤ ድንገት አዲስ ሀሳብ አፍልቆ፣ መልካም ነገር እሰራለሁ ብሎ ማሰብ ከቀናነት አያልፍም፡፡ ቢረፍድም እንኳን ተመሳሳይ ሀሳብ ያለው መሰባሰብ ይኖርበታል፡፡ ልባችን ምንም ያህል ንፁህ ቢሆን ወይ አስቀድመን ስናስብበት የቆየን ያልተዳሰሰ ሀሳብ ከሌለን፣ ወይ አሮጌ ሀሳባችንን በአዲስ አቀራረብ ካላመጣን፣ እንደው በአንድ ጀምበር ሁኔታው አመቺ ስለሆነ በፍጥነት እንለወጣን ብንልም ምኞታችን ይበዛና ተግባሩ ላይ እንሰንፋለን፡፡ ቆይተንም እንወድቃለን፡፡ ስለዚህ ምን ምን ጉዳዮች ያስማሙናልና ወደ ተግባር ያሸጋግሩናል ብሎ ከትንሹ ዕቅድ መነሳት ተገቢ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ያልተመለሱ ጥያቄዎችን በጥሞና መመርመር ዋና ጉዳይ ነው፡፡ እነሱ ላይ አተኩሮ ከስር ከስር በዕቅድ መመለስና እንዲጨበጡ ማድረግ፣ የማይታለፍ እርምጃ ነው፡፡ የተመለሱ የሚመስሉንን ጥያቄዎችም ደግመን መፈተሽ ያስፈልጋል፡፡ ለብ ለብ እንዳይሆኑ፡፡ ለዚህ እንቅፋት የሆኑብንን ጉዳዮች አበጥሮ ማውጣት ተገቢ ይሆናል፡፡ በእኛ አገር “አለባብሰው ቢያርሱ፣ በአረም ይመለሱ” የሚለው ተረት የሁልጊዜ ዕውነት ነው፡፡ አንድም ደግሞ “እርስ በርሱ ሥጋ በኩበት ጠበሱ” የሚለው እውነታ የሚሻል ወይም አመለካከቱ የተለየ ሰው ሳይኖር እንመሳሰላለን በሚል ብቻ አብሮ መዝመት ኋላ ሁኔታው ሲጠራ፣ ከተሰራው ሥራ ውሽልሽልነት ውጤቱ ይታያልና ከወዲሁ ጠንቀቅ ማለት የአባት ነው፡፡
በተደጋጋሚ እንዳወሳነው መንገዶች ሁሉ አልጋ በአልጋ አይደሉም፡፡ እንዲያውም እንደኛ ባለው የፖለቲካ አካሄድ፤ ኮረኮንቹና እሾኻማው ክፍል ሳይበዛ አይቀርም፡፡ አዲስ ሀሳብ የማይጥመው ወገን ይኖራል፡፡ በዱሮው ቋንቋ ወግ - አጥባቂ የሚባለው መሆኑ ነው፡፡ ወንበሩን የተነጠቀው፤ ጥቅሙ የተነካበትና የከመርኩት ሁሉ ተናደብኝ የሚለው ውሎ አድሮ ለሰራው ሁሉ ተጠያቂ እንደሚሆን ስለሚገነዘብ ወይም ስጋት ስለሚኖረው፤ ለህልውናው መታገሉና መፍጨርጨሩ አይቀሬ ነው፡፡ ሆኖም ሶስት ነገሮች ካልተስተካከሉ ሞተሩን ወደ ኋላ መመለስ አዳጋች ነው፡፡ እነዚህም የኃይል ሚዛን፣ የጊዜ ሚዛን እና የነባራዊ ሁኔታ ሚዛን ናቸው፡፡ የኃይል ሚዛን ላዕላይ መዋቅሩ ላይ ካሉት ተዋንያን ወደፊት ልራመድ የሚለውና ወደ ኋላ የሚጎትተው (ያለንበት ሁኔታ ምን አጠፋ? የሚለው) ከሚያደርጉት ፍጭት የሚከሰት ነው፡፡ ይህም ከሂደት እንጂ ከድንገቴ ክስተት የመጣ አይደለም፡፡ የጊዜ ሚዛን ደግሞ ክፉን ከደግ አነፃፅሮ፣ ወቅትን ለክቶ ከሚወሰድ አቋም የሚመነጭ ነው፡፡ “ጊዜው ገና ነው” ወይም “ጊዜው አሁን ነው!” ብሎ የመንቀሳቀስን ዕቅጩነት (Precision) የሚጠይቅ የጥንቃቄ ስሌት ነው። የነባራዊ ሁኔታ ሚዛን ደግሞ ከሁለቱ ከቀደሙቱ ጋር የተሳሰረ ሲሆን፤ ህብረተሰብ በዚህም በዚያም ምክንያት የተጠራቀመ ምሬትና ጥያቄ ሲኖረው፣ ያንን ለማፈንዳት ባመቸው መንገድ ሁሉ ተጠቅሞ ሲያስተነፍሰው የሚመጣ እንቅስቃሴ ውጤት ነው፡፡ ሰለስቱ ሚዛናትን መርምሮ መጓዝ ለብዙ ችግሮች መፍትሔ ይሆናልና አንዘንጋቸው፡፡
“አያሌ አደራዎችን መቀበል ትከሻን ያጎብጣል” ይላሉ አረቦች፡፡ ለብዙኃኑ ደስታ ብለን እሰራለሁ የምንላቸው፣ ቃል የምንገባቸው ሁኔታዎች መልሰው እንዳይጠልፉን ቆም ብለን ማሰብ፣ ውስብስቦቹን ከቀላሎቹ መለየት ያሻናል፡፡ ይሄንን ለመተግበር የሚኖረን ፍጥነት ራሱ ጥንቃቄን ይጠይቃል፡፡ በሰራነው ልንረካ እንችላለን፡፡ ሆኖም ምን ያህል ውሃ የቋጠረና ሥር የሰደደ ስራ ሰርቻለሁ? መሰረቱን በአግባቡ ደልድያለሁ ወይ? ምን ያህል የውጪ ኃይሎች ጣልጋ ገብነት አለብኝ? በቤት ውስጥ ጉዳይ ስጣደፍ፣ የጎረቤቶቼን ነገር እንደምን ይዤዋለሁ? ማህበራዊ መስህብን የመፍጠር አካሄድ ብቻ ላይ ካተኮርኩ ፖፑሊስት (Populist) ያደርገኛል አያደርገኝም? ፍጥነቴን ለመቆጣጠር በተለይ ምን ኃይል መፍጠር አለብኝ? እዚህ ጋ ቁም፣ እዚህ ጋ ሩጥ የሚል አካል አለኝ ወይ? ከስሜታዊነት ከሞቅ ሞቅና ከለብ ለብ ፍጥነት፣ ስክነትን ለመውለድ፤ አቅምንም ላለመጨረስ በብስለት መጓዝ ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ ደግሞ “የእነ ቶሎ ቶሎ ቤት ግድግዳው ሰምበሌጥ”ን ልብ ማለት ይበጃል!


--------------

  በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞንና በደቡብ ክልል ጌዲኦ ዞን ካለፈው ሚያዝያ ወር አንስቶ በተቀሰቀሱ ግጭቶች ከመኖሪያቸው የተፈናቀሉ ዜጎች ቁጥር 970 ሺህ ያህል መድረሱን አለማቀፉ የስደተኞች ድርጅት ትናንት ባወጣው መረጃ አስታውቋል፡፡
በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ በተከሰቱ ግጭቶች ከደቡብ ብሄር ብሄረሰቦች ክልል ጌዲኦ ዞን 822 ሺህ 187፣ ከኦሮምያ ክልል ጉጂ ዞን ደግሞ 147 ሺህ 40 ሰዎች መፈናቀላቸውን ያስታወቀው ድርጅቱ፣ ተፈናቃዮቹ ትምህርት ቤቶችንና የመንግስት ተቋማትን ጨምሮ በተለያዩ ስፍራዎች ተጠልለው እንደሚገኙ አመልክቷል፡፡
አለማቀፉ የስደተኞች ድርጅት ባለፉት ግንቦትና ሰኔ ወራት ባደረገው ጥናት በመላ አገሪቱ 1.7 ሚሊዮን ዜጎች በአገር ውስጥ ተፈናቅለው እንደሚገኙና ከእነዚህም መካከል 1.2 ሚሊዮን ያህሉ በግጭት ሳቢያ የተፈናቀሉ መሆናቸውን ማረጋገጡን ዥንዋ ዘግቧል፡፡


 ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ገበሬ በሬው ይጠፋበታል፡፡ በሬውን ለመፈለግ የመንደሩን ህዝብ እርዳታ ጠየቀ፡፡ መንደሬው ተሰባስቦ ሊያፋልገው ወጣ፡፡ አገሩን አሰሱት፡፡ ከሰው ሁሉ አንድ ሰው ፍለጋው ላይ በጥብቅ የተሰማራ አለ፡፡ ፈልገው ፈልገው በሬው ታሥሮ የተደበቀበት በረት አጠገብ ሊደርሱ ሲሉ ያ ሰው ያከላክላል፡-
“አይ በዚህ በኩል እንኳ ከንቱ ድካም ነው፤ በሌላ በኩል እንሂድና እንፈልጋለን” ይላል፡፡ ፈላጊው ሁሉ ፊቱን በሌላ አቅጣጫ ያዞራል፡፡ አሁንም ፍለጋው በሌለ አቅጣጫ ይቀጥላል፡፡ ብዙ ከፈለጉ በኋላ እዚያው በሬው ያለበት በረት ጋ ይደርሳል፡፡
ያም ሰውዬ፤
“አይ! አሁን በዚህጋ ምን አለና ይፈለጋል?
ኧረ በሌላ በኩል እንሂድ፡፡ ዛሬ ሳናገኘው አንገባ!”
ሌላ አቅጣጫ ይቀየራል፡፡ ይዞሩ ይዞሩና እዚያው በረት ጋ ይደርሳሉ፡፡ በሦስተኛው ማዕዘን በኩል የተደረገውን ሙከራ ያው ሰው፤ “በዚህ በኩል ባንለፋ ጥሩ ነው” ብሎ ፍለጋውን ገታው፡፡
ይኸኔ በሬው የጠፋበት ሰው ነቃ!
ጥቂት እንደተራመዱ አንድ የሚያውቀው መንገደኛ ሰው ሌላው መንደር ይመጣና፤
“ወዳጄ በሬህ ተገኘ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ባለ በሬውም፤ “አዝማሪ ያለውን አልሰማህም እንዴ”
“ምን አለ?” አለና ጠየቀው፤ መንገደኛው፡፡
“ነገሩስ ባልከፋ በሬውን መፈለግ
ግን ዳር እየደረስክ ከዐይንህ ሥር ሲሸሸግ
እንደምን ንብረትክን ልታገኘው አሰብክ
ከሰራቂህ ጋር ተሻርከህ እየዞርክ!”
ይሄኔ ያ አፈላጊ ነኝ እያለ አብሮ እሚዞር ሌባ፤ እንደተነቃበት ገብቶት ድራሹ ጠፋ!
* * *
ከሌቦች ጋር ተሆኖ ሌባ-ሻይ መሆን አይቻልም፡፡ ስለዚህ ውስጥን መመርመርና መፈተሽ የማናቸውም አዲስ የለውጥ ሥርዓት አሀዱ እርምጃ ነው፡፡ ሌብነት ከምዝበራና ከብዝበዛም ባሻገር፡- ሥራን  ማዳከምን፣ የቢሮክራሲውን ሞተር እንዳይሠራ አሻጥር ማድረግን፣ የተዛባ መረጃ መስጠትንና ህዝብን ማደናገርን፤ የነባር-አፍቃሪያንን ጎራ ምሉዕ- በኩለሄ (በሁሉም የተነካ) እንደነበረ የሚያሳይ ማስረጃ ማቅረብን ቅራኔው የማይታረቅ መሆኑ ይፋ እስኪወጣ ድረስ በጥድፊያ ውስጥ ውስጡን መርዝ መርጨትን፣ አዲስ መዋቅር ብቅ ካለ፣ አናት አናቱን መምታትን… ይጨምራል፡፡ በሩሲያ አብዮት ዘመን የፓርላማ ሰዓት አይሠራም ነበር- የክሬምሊን ደወል ከቆመ አገር ምን ዋጋ አላት? እያሉ ክፉኛ መፃረራቸውን ያንፀባርቁ ነበር፡፡  ልባምና ንቁ የሆነ ትውልድ ክፉና ደግ ለይቶ ህዝቡን በደጉ ወገን ማንቃትና ማገዝ አለበት፡፡፡ በአንዳንድ  ወቅት ስሜታዊነት  የህዝብ ጠላት ነው ይላሉ፤ አበው ፈላስፎች፡፡ በተለይም ጩኸትና ሆታ ሲበዛ “ግርግር ለሌባ ይመቻል” የሚለው ተረት ይሠራል፡፡ በዚህ ላይ የውስጥ ቦርቧሪ ከተጨመረበት አደጋና ሥጋት አረበበ ማለት ነው፡፡
“እኔስ መች ኖርኩ፣ እኔስ መች ተወለድኩ ከጠላቶቼ ጋር አብሬ እየዶለትኩ” ያለው ፎካሪ ወዶ አይደለም! ልብ ይሏል፡፡
ደራሲ ዘውዴ ረታ፤ “የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ መንግሥት” በሚለው መጽሐፋቸው፤
“ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሤ በዚያን ዘመን የሥራ ትጋትና ብልህነት ከሚታይባቸው አንዱ ወልደ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስ ሆነው ስላገኟቸው፤ የማንንም ሀሳብ ሳይ ጠይቁ፤ ከውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ዋና ፀሐፊነት አንሥተው ለጥቂት፣ ወራት ልዩ ፀሐፊያቸው በማድረግ የሥራ ጠባያቸውን ካላመዷቸው በኋላ፣ በ1927 ዓ.ም የጽሕፈት ሚኒስቴር ዋና ዳይሬክተር ብለው ሾሟቸው፡፡”.. ለተሿሚው ኃ/ሥላሴ ባደረጉት ንግግር፡-
“ያሳደግኩትን አበባ እኔው ቆርጬ መጣሉ
ከሁሉ የበለጠ የሚያሳዝነኝ ስለሆነ፤
ይህ ሐዘን እንዳይደርስብኝ ተጠንቀቅ” ብለው ነበር፡፡
ከጃንሆይ ተግባርና ንግግር መማር እጅግ ትልቅ አስተውሎትን ያስጨብጣልና ልብ እንበለው! የምንሾማቸው ሰዎች የሥራ ትጋትና “ጨው ሆይ! ብትጣፍጥ ጣፍጥ፤ አለበለዚያ ድንጋይ ነው ብለው ይጥሉሃል” የሚለውን እናስገንዝባቸው፡፡
አሮጌን ሥርዓት ማፍረስ ቀላል ባይሆንም አዲስ ሥርዓት ማነፅ እጅግ ውስብስብ ነው፡፡ “ከአብሮ አደግህ አትሰደድ” የሚል አንደምታም አያጣም! ስለሆነም የሌት ተቀን ልፋትና መስዋዕትነት ጭምር ግድ ይሆናል! ከምንጠራ እስከ አጥር-አጠራ የመቶ ጀምበር ስራ ብቻ አይደል፡፡ “ትርፉን ነግሮ መከራውን ሳይነግረኝ” እንዳንል ውጣ-ወረዱን ከወዲሁ ማወቅ ይበጃል! ‹ሠንሠለቱን ለመበጠስ ከላላው ቀለበት ጀምር› የሚለውን ጥበባዊ መርህ አንዘንጋ፡፡ ደረጃ በደረጃ የምንሠራው ሥራ ደርዝና ብሰለት ይኖረዋል፡፡
እንደ ሩሲያው መሪ እንደ ጎርባቾቭ፤ የግልፅነት ክስተት (ግላስኖስት) ሁሉን በር በረጋግዶ አንድ መወርወሪያ መዝጊያ እንኳ ሳያበጁ  መቅረት ተገቢ አይሆንም፡፡ “ከተናገርክ ፍርጥ፣  ከመታህ ድርግም” ይላሉ የታክቲክ ጠበብት፡፡ አለበለዚያ እሷ ታስራ፣ በሩ ተከፍቶ ተትቶ፣ ሌባ ገብቶ ሲዘርፍ እንዳየችው ውሻ፤ “በራቸውን ሳይዘጉ ሌባ ሌባ ይላሉ” እንዳንል እንሰጋለን፡፡ ስለዚህም፤
“ላገሩ አልሆን ብሎ ሁኔታው ሲጠጥር
ጠጣሩ እንዲላላ የላላውን ወጥር!” እንላለን-ዛሬም ከገሞራው ጋር!

 የኢትዮ-ኤርትራን ግጭትና የሁለቱን አገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መቋረጥ ተከትሎ በግንቦት ወር 1990ዓ.ም የተዘጋው የቀድሞው የኤርትራ ኤምባሲ ከ20 አመታት ያህል በኋላ ነገ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ በተገኙበት በይፋ እንደሚከፈት ይጠበቃል፡፡
ከአዲስአበባ ስቴዲየም ፊት ለፊት የሚገኘው የቀድሞው የኤርትራ ኤምባሲ አስፈላጊው እድሳት እንደተደረገለትና ሁለቱ አገራት ባለፈው ሳምንት ባደረጉት ስምምነት መሰረት በይፋ ተከፍቶ አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምር የመንግስት ኮምዩኒኬሽን ጉዳዮ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሚንስትር አቶ አህመድ ሽዴ ትናንትበሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡
የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ በኢትዮጵያ እያደረጉት ያለውንና ዛሬ የተጀመረውን ይፋዊ የስራ ጉብኝት አስመልክተው አቶ አህመድ በሰጡት በዚሁ መግለጫ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ባለፈው ሳምንት በኤርትራ ባደረጉት ጉብኝት ሁለቱ አገራት ከተስማሙባቸው ጉዳዮች መካከል፣ ኤምባሲዎቻቸውን መልሶ መክፈት፣ የአየርትራንስፖርት እና የስልክ ግንኙነቶችን እንደገናማስጀመር የሚሉት እንደሚገኙበትም አቶአህመድ ሽዴ አስታውሰዋል።