Administrator

Administrator

 ከዕለታት አንድ ቀን አንድ በኑሮው የደላው፤ ሀብቱ የተመቸው፣ እጅግ ቀብራራ ሰው፣ ነበረ፡፡ የሰፈር ሰው ሁሉ ደግና ለተቸገረ ደራሽ ነው ይለዋል፡፡ ወደ ቤተ - ዕምነት ሄዶ ሰባኪው የሚሉትን ይሰማል፡፡
ሰባኪው - በሀልዮ በነቢር በገቢር የተሰራ ሐጢያትን እግዚሐር ይፍታን
ምዕመናን - አሜን!
ሰባኪው - ለተቸገረ እርዱ!
      - በሽተኛ ጠይቁ!
      - ለደሀ መጽውቱ!
      - ሁለት ያለው አንዱን አንድ ለሌለው ይስጥ!
      - የላይኛው ቤታችሁን እምድር ሳላችሁ አብጁ!
      - ፁሙ! ፀልዩ!
      - ትምህርታችሁን ይግለጥላችሁ!
ምዕመናን - አሜን!
ሰባኪ - ከእናንተ የተሻለ የሚኖር ማን አለ?
ምዕመናን - ማንም!
ሰባኪ - ከእናንተ መካከል ሳይበላ የሚያድር ማን አለ?
ምዕመናን - ማንም!
ሰባኪ - ትሰጡት አትጡ!
ምዕመናን - አሜን!
ሰባኪ - በየመንገዱ የወደቁትን ለማሰብ ልቦና ይስጣችሁ!
ምዕመናን - አሜን!
ሰባኪ - የሰማነውን በየልቦናችን ያሳድርብን!
ምዕመናን - አሜን! አሜን!
ሁሉም ወደ የቤታቸው ሄዱ፡፡ ያም ሀብታም ሰው ወደ ቤቱ ለመሄድ መንገድ ጀመረ፡፡
ወደ ቤቱ መሄጃው ላይ አንድ ድልድይ አለ፡፡ እድልድዩ ላይ በግራና በቀኝ በኩል ተቀምጠው የሚለምኑ ሁለት ዓይነ - ሥውር ለማኞች አሉ፡፡ መካከላቸው ሲደርስ ከኪሱ በርካታ ሳንቲሞች አወጣ!
ለማኞቹ - “ጌታዬ አትለፈን! ካለህ አይጉደልብህ! ትሰጠው አትጣ! ትመፀውተው አትጣ! እጅህ እርጥብ ይሁን!” ይሉታል፡፡
ሀብታሙ ሰው ከኪሱ ያወጣቸውን ሳንቲሞች በሁለት እጆቹ ይዞ አንኳኳቸው፡፡ ሿ! ሿ! ሿ! አደረጋቸው፡፡ ሁለቱ ዐይነ - ስውር ለማኞች በጣም ጎመጁ፡፡ ከአሁን አሁን መጥቶ ይሰጠናል ብለው ሲጠብቁ, ሳንቲሞቹን መልሶ ኪሱ ከቶ፤
“ተካፈሉ!” ብሎ ሄደ፡፡
በወዲህ ወገን ያለው ለማኝ; “ያኛው ተቀብሏል፤ ያካፍለኛል” አለ፡፡
በወዲያ በኩል ያለውም ለማኝ፤
“እሱ ተቀብሏል፣ ያካፍለኛል!” አለ፡፡
ሁለቱም ምንም ሲያጡ ተነስተው አንዱ; “ስጠኝ! የሰጠንን አካፍለኝ!` ሌላውም; “ላንተ ነው የሰጠህ አካፍለኝ!”
`አንተ ወስደሃል … አንተ ወስደሃል” እየተባባሉ፤ ድብድብ ጀመሩ፡፡
ሀብታሙ ሰው; ከሩቅ ሆኖ ከት ብሎ ሳቀባቸውና ወደ ቤቱ ሄደ!
***
እኛ ኢትዮጵያውያን ደግ፣ እንግዳ ተቀባይ፣ ለተቸገረ ደራሽ፣ ተዛዛኝ … እንባላለን፣ እንጂ ጭካኔያችን ለከት የለውም! ውስጣችን አልተፈተሸም፡፡ አልተመረመረም! በሰብአዊነት ሽፋን የምንኖር ኢ-ሰብአዊዎች ነን! ፈዋሽ ሀኪም አልተገኘልንም እንጂ የውስጥ ደዌ አለብን - ጭካኔ! እንዋደዳለን እንላለን እንጂ ውስጣችን በጭካኔ አባዜ የተሞላ ነው! የመሀይምነታችንና የአረመኔነታችን (Barbarism) መጠን ገና አልታወቀም - አልተጠናንም! እርግጥ ሁላችንም ላንሆን እንችላለን እንጂ የክፋታችን ልክ ይህ ወሰንህ፣ ይህ ዲካህ የሚባል አይደለም፡፡ አያምጣው እንጂ ክፉ ጊዜ ቢመጣ፣ እርስ በርስ ሊያበላላን ይችላል! ነፃነት ይከብደናል! መከራ ከመልመዳችን የተነሳ ነፃነት ሸክም ይሆንብናል፡፡ ድህነታችን የሀብት ብቻ ሳይሆን የአዕምሮም ነው! የልቡናም ነው! ደግ ጊዜ ያምጣልን እያልን፣ ደጉን ጊዜ ገፍተን እንጥላለን! ይሄ ኃይለኛ የልቡና ቀውስ ነው! አዎንታዊ ነገር የማይጥመን ከሆነ፣ አሉታዊው ነገር በደም ጎርፍ ያስተጣጥበናል!
ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን በቴያትሩ እንዳስቀመጠው፤
“ሞትን ለሚሻ ሞትን ነው መንፈግ! ህይወትንም አለመቸር! እማህል ቤት ነው የሰው ልጅ ጥቅም የሚሰጥ! ሰው ሆኖ ካሹት፣ ጥቅም የማይሰጥ የለም!” ይለናል፡፡ ለዚህ ፀሐፊ፣ የአበሻ ውስጠ ነገር ዱሮ ነው የገባው ማለት ነው!
ያም ሆኖ “በርኩቻው ማህል ፀጥ ብለህ ለመጓዝ ሞክር” ይላል፤ የጥንቱ የጠዋቱ የዴዚዴራታ ምክር! ምክሩ ከገባን ዓለም በውካታ የተሞላች ናት - አንተ ግን ተረጋግተህ ተጓዝባት ማለት ነው፡፡ መረጋጋት፣ ማረጋጋት፣ ሁኔታዎችን በሰከነ ዐይን ማየት፤ የበሳል ሰው መርህ ነው፡፡ “በካፊያው ከተረበሽክ የዶፉ ዝናብ ጊዜ ምን ይውጥሃል?” ይላሉ አበው፡፡ ህዝባችንን ማሳወቅና ማስተማር፣ መሰረታዊ ጉዳያችን መሆን አለበት፡፡ በክፋት፣ በጭካኔና በአረመኔያዊነት (Barbarism) እና በህዝባዊ እምቢተኝነት (Civil disabidience) መካከል፤ የገደል ያህል ልዩነት አለ፡፡ የፊተኛው የኃላ ቀርነት፣ የኋለኛው የአዋቂነት አስተሳሰቦች ናቸው፡፡ በመሰይጠንና በመሰልጠን መካከል ያለውን አደጋ እናስተውል፡፡ የዱሮ ፍልስፍናም ቢሆን “ህግ የማይገዛውን ነፃነት፣ ኃይል ይገዛዋል” የሚለውን አባባልም እንደገና ማውጠንጠን ግዴታ ሊሆን እንደሚችል አንዘንጋ፡፡ “ጥንቃቄ ሲጠብቅ ፍርሃት ይሆናል” የሚለውንም አንርሳ፡፡ ዞሮ ዞሮ የሚመለከተውና ኋላፊነቱ የሚሰማው ክፍል የሚያደርገውን ያውቃል ብለን እንገምታለን - “እኔ ተጎድቼ ባመጣሁበት ውሰደው” ይላል ጮሌ ነጋዴ፡፡
ሀገራችን ሾተላይ ያለባት ይመስል ፅንስ ይጨነግፍባታል፡፡ ማስወረድ ልማድ ሆኖባታል፡፡ አሮጊው እንቅፋት አዲስ እንቅፋት እየፈለፈለ ያሽመደምዳታል፡፡ “እኔ ስወለድ ነው የሳቅ ጀምበር የጠለቀችው” የሚል ኢትዮጵያዊ እንዳይበዛ፤ ልባም ልባሞቹ ሰዎች መመካከር አለባቸው፡፡ “ገዢ እንጂ መሪ አያምርብንም” እንዳለው አፍሪካዊው ፀሐፊ፤ በግድ የገዢ ያለህ እያልን እንዳንፀልይ ምህረቱን ይላክልን፡፡ ውድቀትን ማቀድ አልፎ አልፎ ያዋጣል ብንልም፣ መነሻችን ጨለምተኝነት ከሆነ፣ ከ“ሁሉም ይውደም ፍልስፍና” (nhilism) አባዜ አይተናነስም! “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል” እንዳለችው እንስሳም፤ የአገር ጨለማን መባጀት ክፉ እርግማን ነው! የየዓይነቱን እርግማን በበቂ አይተናልና አዲስ እርግማን ፍለጋ መባቸር ከንቱ መላላጥ ነው፡፡ “ከመርገምት ሁሉ የከፋው መርገምት፤ ቋንቋ ለቋንቋ መጠፋፋት ነው!” ይላል ገጣሚው፡፡ መግባባት እንዳይጠፋብን አሳቢዎቻችንን (Thinkers) እናዳምጥ እንሰማማ!! እርስ በርስ እንናበብ፡፡ መናበባችንን ይባርክልን ዘንድ ቀና እንሁን፡፡ አገራችን ኢትዮጵያ ከእንግዲህ “ትወልዳለች እንጂ አታሳድግም” መባሏ መቆም አለበት፡፡ የበቀሉ ዕድሎች እንዳይጠወልጉ እንንከባከባቸው! እውቀታችንንና አቅማችንን ሁሉ አፍንጫችን ሥር ባለው ጉዳይ ላይ ሳይሆን ትልቁን ስዕል አገርን (The Bigger Picture) ማየት ላይ እናውለው፡፡ የግለሰቦችን ምንነት ከአጠቃላዩ ህዝብ ህልውና ለይተን እንይ! ዛሬም ትምህርታችንን ይግለጥልን!!  

 እነዚህ አ/ አበባ ውስጥ የሚገኘው አዲሱ የሲኤምሲ - መሪ የ40/60 ኮንዶሚኒየም ሳይት ማራኪ ህንጻዎች ናቸው፡፡ ህንጻዎቹ ከሩቅ ላያቸው ማራኪ ገጽታን ቢላበሱም፣ ዙሪያቸው ግን ለከፋ የጤና ችግር በሚያጋልጥ ቆሻሻ የታጠረ ነው፡፡ያማሩ የመኖሪያ ቤቶችን መገንባቱ በጎ ሆኖ፣ ነዋሪዎችን ነጋ ጠባ በአስቀያሚ ጠረን ለሚያማርር የቆሻሻ ክምርና የተበከለ ፍሳሽ መፍትሄ መስጠትስ የማን ሃላፊነት ይሆን? የሚያምሩ ህንጻዎችን መገንባት፣ የሚያማርሩ የቆሻሻ ተራራዎችን በማፍረስ ይታገዝ!

 የአለማችንን ከተሞች የመሰረተ ልማት አውታሮች መሟላት፣ የጸጥታና መረጋጋት፣ የጤና አገልግሎት ጥራት፣ የትምህርት አሰጣጥና ሌሎች መስፈርቶች ተጠቅሞ በመገምገም፣ በየአመቱ ደረጃ የሚሰጠው ኢኮኖሚስት ኢንተለጀንት ዩኒት የተባለው ተቋም፣ ከሰሞኑም የ2018 ለኑሮ ተስማሚና ምቹ የአለማችን ምርጥ ከተሞችን ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ የኦስትሪያዋ ቬና በአንደኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች፡፡
ላለፉት ሰባት ተከታታይ አመታት ለኑሮ ምቹ በመሆን ከአለማችን ከተሞች በቀዳሚነት የዘለቀቺው የአውስትራሊያዋ ሜልቦርን ዘንድሮ ወደ ሁለተኛ ደረጃ ዝቅ ማለቷን የዘገበው ሲኤንኤን፤ የጃፓኗ ኦሳካ በሶስተኛ ደረጃ ላይ መቀመጧን አመልክቷል፡፡
የካናዳዋ ካልጋሪ፣ የአውስትራሊያዋ ሲድኒ፣ የካናዳዋ ቫንኮቨር፣ የጃፓኗ ቶኪዮ፣ የዴንማርኳ ኮፐንሃገንና የአውስትራሊያዋ አዴላዴ እንደ ቅደም ተከተላቸው ከአራተኛ እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡ ተቋሙ በዘንድሮው ለኑሮ ምቹ የአለማችን ከተሞች ዝርዝር ውስጥ 140 የተለያዩ የአለማችን አገራት ከተሞችን ያካተተ ሲሆን፣ አውስትራሊያና ካናዳ እያንዳንዳቸው ሶስት ከተሞችን ማስመዝገብ መቻላቸውንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
በጦርነት የፈራረሰቺዋ የሶርያ መዲና ደማስቆ በዘንድሮው የአለማችን ከተሞች ዝርዝር ውስጥ በመጨረሻው ደረጃ ላይ የተቀመጠች ለኑሮ እጅግ አዳጋችና አስቸጋሪ የአለማችን ከተማ ስትሆን፣ የባንግላዲሽዋ ዳካ እና የናይጀሪያዋ ሌጎስ 139ኛ እና 138ኛ ደረጃን መያዛቸውን ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

 በቱርክ በመሬት መንቀጥቀጥ 30 ሺህ ዜጎች ሊሞቱ እንደሚችሉ ተነግሯል

    በህንድ ለቀናት የዘነበው ሃይለኛ ዝናብ ያስከተለውና ባለፉት የአገሪቱ 100 አመታት ታሪክ እጅግ የከፋው እንደሆነ የተነገረለት የጎርፍ አደጋ፤ 44 ሰዎችን ለሞት  መዳረጉ ተነግሯል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ በደቡባዊ ህንድ በምትገኘው ኬራላ ግዛት የተከሰተው የጎርፍ አደጋ፣ በአስር ሺህ የሚቆጠሩ ነዋሪዎችን ከመኖሪያ ቤታቸው ማፈናቀሉን የዘገበው ዘ ኢንዲፔንደንት፤ ከ50 ሺህ በላይ የአካባቢው ነዋሪዎች በመጠለያ ካምፖች ውስጥ እርዳታ እየተደረገላቸው እንደሚገኙም አመልክቷል፡፡
የጎርፍ አደጋው በተለይ ህጻናትንና ሴቶችን ክፉኛ ማጥቃቱን የጠቆመው ዘገባው፤ የትራንስፖርት አገልግሎቶችን ማቋረጡንና በርካታ ቤቶችን፣ የመሰረተ ልማት አውታሮችንና ሰብሎችን ማውደሙን ጠቅሶ፣ በአደጋው ተጎጂ ለሆኑ ዜጎች የአስቸኳይ ጊዜ እርዳታና ህክምና ለመስጠት ርብርብ እየተደረገ እንደሚገኝም አክሎ ገልጧል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ የቱርክ የአደጋ ቁጥጥር ኤጀንሲ፣ በኢስታንቡል አካባቢ ይከሰታል ተብሎ የሚጠበቀው ከፍተኛ የመሬት መንቀጥቀጥ፣ በከተማዋ የሚኖሩ 30 ሺህ ዜጎችን ለሞት ሊዳርግ እንደሚችል ባወጣው መግለጫ ማስጠንቀቁን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡ ኤጀንሲው ከትናንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ እንዳለው፤ በኢስታንቡል በሬክተር ስኬል 7.5 የሚገመት የመሬት መንቀጥቀጥ ሊከሰት እንደሚችል ያስጠነቀቀ ሲሆን፣ ነዋሪዎች ተገቢውን ዝግጅት እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርቧል፡፡
የመሬት መንቀጥቀጡ 50 ሺህ በሚሆኑ ሰዎች ላይ ከፍተኛ የመቁሰል አደጋ ሊያስከትል እንደሚችል ያስጠነቀቀው ኤጀንሲው፤ 49 ሺህ ያህል ህንጻዎችንም ሊያፈራርስና 2.4 ሚሊዮን ዜጎችን ቤት አልባ ሊያደርግ እንደሚችልም አስታውቋል፡፡

 የአለማችን የሶል ሙዚቃ ንግስት እንደሆነች የሚነገርላት አሜሪካዊቷ ድምጻዊት አሪታ ፍራንክሊን፣ በካንሰር ህመም በ76 አመቷ ከትናንት በስቲያ ከዚህ አለም በሞት መለየቷ ተዘግቧል፡፡
ከስድሳ አመታት በላይ በሚዘልቀው የሙዚቃ ህይወቷ፣ በአለማቀፍ የሙዚቃ መድረክ፣ በሶል ሙዚቃ ዘርፍ አብሪ ኮከብ ሆና የዘለቀቺው አሪታ ፍራንክሊን፤ ላለፉት ስምንት አመታት በካንሰር ህመም ስትሰቃይ እንደነበር ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
በታላቁ የግራሚ ሽልማት ለ18 ጊዜያት ያህል ተሸላሚ የሆነቺው አሪታ ፍራንክሊን፣ በሙዚቃ ስራዎቿ በርካታ አገር አቀፍና አለማቀፍ ሽልማቶችን ማግኘቷን የጠቆመው ዘገባው፤ የፕሬዚዳንቱን የነጻነት ሜዳይ ጨምሮ በርካታ የክብር ሽልማቶችን ማግኘቷንም አመልክቷል፡፡
አሪታ ለመጨረሻ ጊዜ በመድረክ ላይ ስራዎቿን ያቀረበቺው ባለፈው ህዳር ወር፣ በኒውዮርክ በተዘጋጀ የሙዚቃ ኮንሰርት ላይ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ ህልፈተ ህይወቷ መሰማቱን ተከትሎ በርካታ ዝነኞችና አድናቂዎቿ በማህበራዊ ድረገጾች ሃዘናቸውን በመግለጽ ላይ እንደሚገኙም ጠቁሟል፡፡

  ታጣቂዎች 2 ሺህ ስደተኞችን ከመጠለያ አባርረዋል

    የሊቢያ ፍርድ ቤት የቀድሞው የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሙአመር ጋዳፊ ደጋፊ የነበሩና ከሰባት አመታት በፊት በመዲናዋ ትሪፖሊ ለተቃውሞ ሰልፍ የወጡ ዜጎችን በመግደል በተከሰሱ 45 ሰዎች ላይ የሞት ፍርድ ማስተላለፉ ተዘግቧል፡፡
ለተቃውሞ የወጡ ዜጎችን ገድለዋል በሚል ክስ ከተመሰረተባቸው 128 ሊቢያውያን መካከል ዘጠና ዘጠኙ ጥፋተኛ ሆነው መገኘታቸውን የዘገበው ዥንዋ፤ ጉዳዩን ሲከታተል የቆየው የትሪፖሊ ፍርድ ቤት ባለፈው ረቡዕ በዋለው ችሎት በ45ቱ ላይ የሞት ፍርድ ውሳኔውን ማስተላለፉን አመልክቷል፡፡
እ.ኤ.አ በ2011 ነሃሴ ወር ላይ የቀድሞውን ፕሬዚዳንት ሙአመር ጋዳፊን ስርዓት ለመቃወም በመዲናዋ ትሪፖሊ አደባባይ የወጡ በርካታ የአገሪቱ ዜጎች በጋዳፊ ደጋፊዎች በአደባባይ አንገታቸውን እየተቀሉ መገደላቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ የአገሪቱ ታጣቂ ቡድኖች የጋዳፊ ደጋፊ ናቸው ያሏቸውን 2 ሺህ ያህል የአገር ውስጥ ተፈናቃይ ስደተኞችን ትሪፖሊ ከሚገኝ የመጠለያ ካምፕ ማባረራቸውን የተመድ የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን አስታውቋል፡፡
ተቋሙ ከትናንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ እንዳለው፤ በሊቢያ 192 ሺህ ያህል የአገር ውስጥ ተፈናቃዮች ለአመታት የከፋ ኑሮን በመግፋት ላይ የሚገኙ ሲሆን በተለይም ከአናሳ ጎሳ የተወለዱ ሊቢያውያን በታጣቂዎች ከፍተኛ በደል እንደሚፈጸምባቸው አመልክቷል፡፡

 “የአዲሲቷ ኢትዮጵያ ታዳጊዎች ፌስቲቫል” የተሰኘ በታዳጊዎች የበጎ አድራጎት የባህል፣ የኪነ ጥበብ፣ የተሰጥኦ ማሳያ፣ የግብይት፣ የቁጠባ፣ የጨዋታና የውድድር ፌስቲቫል ሊካሄድ ነው፡፡
በዚህ ፌስቲቫል ላይ ታዳጊ ወጣቶች ታላቅ ራዕይ ያላቸው፣ በራሳቸው የሚተማመኑ፣ በአገራቸው ምርት የሚኮሩ፣ በበጎ አድራጎት ተግባራት ላይ የሚሳተፉ እንዲሆኑ የሚያበረታቱ ዝግጅቶች እንደሚካሄዱ ተገልጿል፡፡
የፌስቲቫሉ አዘጋጆች በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት፤ ፌስቲቫሉ ታዳጊዎች ቁምነገርን በቀልድና በጨዋታ በማዋዛት የሚገነዘቡበት፣ የቁጠባ ባህላቸውን የሚያዳብሩበት የግል ተሰጥኦዋቸውን በማሳየት የሚወዳደሩበትና የሚሸለሙበትን ዝግጅቶች አካትቷል፡፡
ልደታ አካባቢ በሚገኘው የልደታ መርካቶ ገበያ አዳራሽ ውስጥ ከነሐሴ 20 እስከ ጳጉሜ 2 ቀን 2010 ዓ.ም በሚካሄደው በዚሁ ፌስቲቫል ላይ የተለያዩ የበዓል ዝግጅቶች፣ የሰርከስ ትርዒቶችና ሌሎችም በርካታ የመዝናኛ ፕሮግራሞች እንደሚቀርቡ አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡ ፌስቲቫሉን ሻክርክስ ንግድና ኤቨንትስ ማኔጅመንት ከተለያዩ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ጋር በትብብር ያቀርበዋል ተብሏል፡፡  

 “ሰውኛ ፕሮዳክሽን ኢንተርቴይመንት” ከጉዞ አድዋ፣ ከኢጋ ሚዲያና ኮሚዩኒኬሽንና ከአዲስ አበባ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ጋር በመተባበር፤ ዛሬ ከቀኑ 7፡30 ጀምሮ የእቴጌ ጣይቱን፣ የአፄ ምኒሊክንና የፊታውራሪ ገበየሁን ልደት በልዩ ልዩ ዝግጅቶች እንደሚያከብር አስታወቀ፡፡
በዓሉ የአዲስ አበባ ከንቲባ ኢ/ር ታከለ ኡማ በሚታደሙበት በእንጦጦው የአፄ ምኒልክ ቤተ መንግስት የሚከበር ሲሆን በልዩ ልዩ ኪነ ጥበባዊና ታሪካዊ ዝግጅቶች ተጀምሮ አዲስ አበባ የሚገኙ ዋና ዋና ታሪካዊ ሀውልቶችን በመጎብኘት እንደሚጠናቀቅ ያስታወቀው “ሰውኛ ፕሮዳክሽን ኢንተርቴይንመንት” ነው፡፡

 · ያለ ዶ/ር ዐቢይ፤ የደቡብ ሱዳን ስምምነት አይታሰብም
   · የውጊያ ቀጠናዎችን የልማት ጣቢያ እናደርጋቸዋለን
   · ሁለቱን አገራት የሚያገናኝ የባቡር ሃዲድ ይዘረጋል

     ሚስተር ጄምስ ፒተር ሞርጋን፣ በኢትዮጵያና በጅቡቲ የደቡብ ሱዳን አምባሳደር ናቸው፡፡ የምስራቅ አፍሪካ በይነ መንግስታት (ኢጋድ) እና የአፍሪካ ህብረት እንዲሁም የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) ተወካይ በመሆንም እያገለገሉ ይገኛሉ፡፡ በእርስ በርስ ጦርነት ለዓመታት ስትታመስ የቆየችው ደቡብ ሱዳን፤ በመሪዎቿ ስምምነት አለመድረስ የተነሳ ማጣት በመቶ ሺዎች የሚሰሉ ዜጎቿን ለስደትና እንግልት ዳርጋለች፡፡ ባለፈው ሳምንት ግን ታሪክ የተለወጠ ይመስላል፡፡
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሳልቫኪርና ተቃዋሚያቸው ዶ/ር ሪክ ማቻር ጦርነት አቁመው፣ በአገራቸው ላይ በሰላም ለመስራት በካርቱም ስምምነት ተፈራርመዋል። ስምምነቱን ተከትሎ በኢትዮጵያ የሚገኙት አምባሳደሩ ትላንት ረፋድ ላይ ለአገር ውስጥና ለውጭ አገር ጋዜጠኞች በደቡብ ሱዳን ኤምባሲ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ በመግለጫው ላይ የተገኘችው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ከዚህ ቀደም የተደረጉት ስምምነቶች ለምን እንዳልተሳኩ፣ የአዲሱ ስምምነት አስተማማኝነት ምን ያህል እንደሆነ፣ በኢትዮጵያና በደቡብ ሱዳን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ዙሪያና ሌሎች ጥያቄዎች አንስታ አነጋግራቸዋለች፡፡


    ኢትዮጵያ ሲመጡ የመጀመሪያዎ ነው ወይስ ከዚሀ በፊት ያውቋታል?
ኢትዮጵያ ስመጣ የመጀመሪያዬ ነው፤ ኢትዮጵያን ሳውቃት ግን የመጀመሪያዬ አይደለም፡፡ ኢትዮጵያን የማውቃት ባልሳሳት በ1974 ዓ.ም ነበር፡፡ ያን ጊዜ እድሜዬ ምናልባት ከ8-10 ዓመት ባለው ውስጥ ይሆና።፡ ገና የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤት ተማሪ ነበርኩኝ፡፡ ንጉስ ኃይለሥላሴ ጁባን ለመጎብኘት ሲመጡና ሳያቸው የመባረክ ስሜት ነበር የተሰማኝ። ከኤርፖርት እስከ ጁባ ስታዲየም ድረስ ነበር አቀባበል ያደረግንላቸው፡፡ እስካሁን ድረስ ከውስጤ ያልጠፋውና የመሰጠኝ የንጉሠ ነገሥት ኃይለሥላሴ አለባበስ ነው፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ነው ኢትዮጵያን ማወቅ የጀመርኩት፡፡ ይሄ ደግሞ በጣም ረጅም ጊዜ ነው፡፡ ሆኖም ከጃንሆይ እስከ ቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ድረስ የነበሩት የኢትዮጵያ መሪዎች ሲደግፉንና ሲረዱን ነው የቆዩት፡፡ በዚህ ምክንያት ኢትዮጵያን በደንብ እናውቃታለን። እዚህ በመምጣቴ ደስተኛ ነኝ፡፡ ቤቴ እንዳለሁ ይሰማኛል፡፡ የኢትዮጵያ የተለያዩ ብሔረሰቦች ዳንሶች ደስ ይሉኛል፡፡
የዛሬው ጋዜጣዊ መግለጫ ዓላማው ምንድነው?
ዋና አላማው ደቡብ ሱዳን በመሪዎቹና በተቃዋሚዎቹ ምክንያት የእርስ በእርስ ጦርነት ውስጥ ገብተን፣ ሰላም አጥተን ከርመናል፡፡ ይህንን ችግር ለመፍታትና አገራችን ወደ ሰላም እንድትመጣ ደግሞ ኢትዮጵያ ብዙ ደክማና ብዙ ጥረት አድርጋ፣ በመጨረሻም ፕሬዚዳንት ሳልቫኪርና ተቃዋሚው ምክትላቸው ዶ/ር ሪክ ማቻር ስምምነት ላይ ደርሰው፣ ባለፈው ሳምንት ጦርነት ለማቆምና ወደ ሰላማዊ መንገድ ለመምጣት ካርቱም ላይ ስምምነት ተፈራርዋል፡፡ ይህንን ትልቅ ስኬት ለኢትዮጵያና ለሌሎች ዓለም አቀፍ ሚዲዎች ለማብሰርና ኢትዮጵያን ለማመስገን ነው ጋዜጣዊ መግለጫው የተዘጋጀው፡፡ ለዚህ የእርስ በርስ ጦርነት ማብቃት የወቅቱ የኢጋድ ፕሬዚዳንትና የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ከፍተኛ ስራ ሰርተዋል፤ እናመሰግናል። በቀጣይ ይህንን ስምምነት በጁባም በአዲስ አበባም በደማቅ ሥነ ስርዓት እናከብረዋለን፡፡
መቼ ነው የሚከበረው?
በቅርቡ ይሆናል፡፡ አሁን ስምምነቱን ያፈራረመው ቡድን አንዳንድ ሞዳሊቲዎችን በመጨረስና የጊዜ ፍሬሙን በመስራት ላይ ይገኛል፡፡ ያንን ሰርተው ሲጨርሱ በዚህ ወር አጋማሽ ወይም በወሩ መጨረሻ በደማቅ ሁኔታ በማክበር፣ ደስታችንን ለመላው አፍሪካና ለመላው ዓለም ማሳየት እንፈልጋለን፡፡
በአገራችሁ ላይ ሰላም ለማስፈን በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ ስምምነቶች ተፈራርማችሁ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ ለምን ነበር ያልተሳካው? የአሁኑስ ስምምነት ምን ያህል አስተማማኝ ነው ይላሉ?
እውነት ነው! እንዳልሽው የተለያዩ ስምምቶች ተደርገው አልተሳኩም፡፡ ለምሳሌ በ2015 የተደረገውን ስምምነት እንውሰድ፡፡ ይህ ስምምነት ያልተሳካበትን ምክንያት ልንገርሽ፡- አፍሪካ በአምስት ሪጅን ተከፋፍላለች፡፡ የምስራቅ አፍሪካ የቀንዱ አካባቢ አባል አገራት ድርጅት “ኢጋድ” ነው፡፡ የኢጋድ የወቅቱ መሪ ኢትዮጵያ ናት፡፡ የደቡባዊው የአፍሪካ ክፍል “ሳዲክ” ይሰኛል፡፡ “ኢኮዋስ” ደግሞ የምዕራብ አፍሪካ አገራትን የሚመለከት ጉዳይን የሚመራና የሚከታተል ነው፡፡ የሆነ ሆኖ የምስራቅና የቀንዱ አካባቢ አገራትን ችግር ለመፍታት፣ የምስራቅ አፍሪካ በይነ መንግስታት ድርጅት (ኢጋድ) በቂና ጠንካራ ነው፡፡ ነገር ግን እንደነ ሳዲክና ኢኮዋስ ያሉት ድርጅቶች እንዲሁም እንደነ አውሮፓ ህብረት፣ አሜሪካን፣ ኖርዌይንና ብሪታንያን የመሳሰሉ አገራት ጣልቃ ገብነት ነገሩን ሁሉ አበለሻሸው፡፡ የጉዳዩ ባለቤት ያልሆኑ አካላት ባሳደሩት ጫናና ጣልቃ ገብነት ደቡብ ሱዳንናውያን እርስ በእርሳችን መስማማት አልቻልንም፡፡ በጣም አስቸጋሪ ጉዳይ ሆነ፡፡ ተስፋ ቆርጠን በነበርንበት ጊዜ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ ወደ ስልጣን መጥቶ፣ የእኛን ጉዳይ ለምን እንዳልተሳካ ሲመረምር፣ የጣልቃ ገብነቱ ጉዳይ እንቅፋት እንደሆነ ተረዳ፡፡ ይሄ ጣልቃ ገብነት እስካለ ደረስ ደቡብ ሱዳንና ዜጎቿ በፍፁም ወደ ሰላም አይመጡም በማለት፣ በኢጋድ አደራዳሪነት ብቻ ስምምነቱ ተካሄደ፡፡ ራሳቸውን ትሮይካ (Troika) ብለው የሚጠሩት አውሮፓዊያን፣ አሜሪካውያንና ሌሎች ቡድኖች፣ ደቡብ ሱዳን ሰላም እንድትሆን ሳይሆን ጦርነቱ እንዲቀጥል ነው የሚፈልጉት፡፡
በደቡብ ሱዳን ከሚካሄደው ጦርነት ምን የሚያተርፉት አለ?
የሚያተርፉትን የሚያውቁት እነሱ ናቸው፤ ነገር ግን ጦርነቱ እንዲቀጥል ይፈልጋሉ፡፡ መጀመሪያ ችግሩን ካልተረዳችሁት መፍታት አትችሉም ብለን ብዙ ጊዜ ገልፀንላቸዋል፤ ነገር ግን እኛን ሊያዳምጡን አይፈልጉም፡፡ ዶ/ር ሪክ ማቻር አዲስ አይደለም፤ እሱ በ1991 ዓ.ም ለዶ/ር ጆን የችግር መንስኤ እንደ ነበር ይታወቃል፡፡ በ2013ም ሆነ በ2016ም የችግር መንስኤ ነበር፡፡ ይሄንን ነገር ለእኛው ተዉልንና እኛው እንፍታው ብንልም፣ ሊሰሙን ሊያደምጡን አይፈልጉም፡፡ ደቡብ ሱዳንም በነዚህ አገራት ጣልቃ ገብነት እርስ በርስ ስትባላ፣ ሀብቷን ስታወድም፣ ህዝቧን ለሞትና ለስደት ስትዳርግና በኪሳራ ስትጓዝ ቆይታለች። ትሮይካዎች የአገሪቱ ህዝብ 98 በመቶ የመረጠውን መሪ በማስወገድ፣ የአገዛዝ ለውጥ ለማድረግ ሲጥሩ ነበር፡፡ ያን ጊዜ ህዝቡ በአደባባይ ሰልፍ ተቃውሞ አሰምቷል። የደቡብ ሱዳን ህዝብ ትሮይካዎች የሚሰሩትንም ተንኮል ያውቃሉ፡፡ ፕሬዚዳንታቸውንም ያውቃሉ። በዚህ ምስቅልቅል የደቡብ ሱዳን ህዝብ ለከፍተኛ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ቀውስ ተዳርጓል፡፡ ኑሮው ተቃውሷል፡፡ በብዛት ተሰድዷል፡፡
በሶማሊያም በእኛም ዘንድ ችግር በነበረ ጊዜ የኢጋድ አባል አገራት ችግሩን ለመቆጣጠር የኢኮኖሚ ችግር ስለነበረባቸው አልቻሉም፡፡ ይህንን ክፍተት በመጠቀም ትሮይካዎች ሁሉን ነገር ስፖንሰር እያደረጉ፣ ችግር ሲያባብሱ ነው የኖሩት፡፡ ጉዳዩን ወደ ኢሲኤ የስብሰባ አዳራሽ ይወስዳሉ፤ ቁርስ፣ ምሳና ቡና በማዘጋጀት፣ ለነዚህ ቡድኖች የአየር ትኬት በመግዛት ያስመጧቸውና ሃይ ሃይ ብለው ይሸኟቸዋል። በዚህ ዓይነት አገራቱ ዘላቂ የሰላም መፍትሄ ሊያገኙ አልቻሉም፡፡ አላማውን ጠለፉት (ሀይጃክ አደረጉት)፡፡ ሥለ ህግ የበላይነት፣ ስለ ሰብአዊ መብት ያወራሉ፡፡ በአገራት መካከል የተነሳን ጦርነትና እልቂት ግን አያስቆሙም፡፡ አንድ አገሩ ውስጥ የእርስ በርስ ጦርነት ያለበት መሪ (አገር)፤ ስለ ሰብአዊ መብትና ስለ ህግ የበላይነት ብትነግሪው እንዴት ያዳምጥሻል፡፡ አገሩ ላይ ለተነሳው እሳት አስቸኳይ ማጥፊያ መንገድ ብትነግሪው ግን ሄዶ እሳቱን ያጠፋና፣ ከዚያ ስለ ሰብአዊ መብትና ስለ ህግ የበላይነት ይሰራል። ትሮይካዎች ግን ሲቀልዱና ሰው ሲያባሉ ነው የኖሩት፡፡ የደቡብ ሱዳንም ህዝብ በሰላም መኖር እየቻለ፣ በእነሱ ሲሰቃይ ነው የኖረው። ይሄው ዶ/ር ዐቢይ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትርና የኢጋድ ፕሬዚዳንት ሆነ፡፡ ችግሩን ተረዳ፡፡ ያለማንም ጣልቃ ገብነት የችግሩን ባለቤቶች አደራደረ፡፡ አወያየ፡፡ ጦርነታችን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ቆመ፡፡ ተመልሶ ይመጣል የሚል እምነት የለኝም። ዶ/ር ዐቢይ በጣም ስማርት በሆነ መንገድ ነው፣ እነ ትሮይካ ደቡብ ሱዳንን ሊረዱ እንደማይችሉ ገልፆ፤ ጉዳዩን በካርቱም ጨረሰው፡፡ የትሮይካ አባል አገራት ሰዎች ወደ ካርቱም ዝር እንዳይሉ ተደርጎ፣ የደቡብ ሱዳን ተቀናቃኞች በቂ የሆነ ጊዜ ወስደው፣ እርስ በእርሳቸው በደንብ ተነጋግረው፣ እንዲስማሙ ነው ዶ/ር ዐቢይ ያደረገው፡፡ እጅግ በጣም ብልህና በግጭት አፈታት ለደቡብ ሱዳን ብቻ ሳይሆን ለመላው አፍሪካን እንዲሁም ለአለም ምሳሌ የሚሆነን ነው። ፕሬዚዳንት ሳልቫኪርና ዶ/ር ሪክ ማቻር ስምምነት ላይ ሲደርሱ፣ እኔም ካርቱም ነበርኩኝ፡፡ ህዝቡ በደስታ ሲደንስና ሲስቅ ነበር፡፡ ፕሬዚዳንት ሳልቫኪር ከካርቱም ጁባ ሲገቡ፣ ህዝቡ በደስታና በዳንስ አጅቦ በድምቀት ነው አቀባበል ያደረገላቸው፡፡ በርካታ ህዝብ ነበር ለአቀባበል የወጣው፡፡ በአጠቃላይ ዶ/ር ዐቢይ ወደ ስልጣን ባይመጣ፣ ደቡብ ሱዳን ወደ ስምምነት ልትመጣ ቀርቶ ጭራሽ ሙሉ ለሙሉ ትወድም ነበር፡፡ ስለዚህ በዶ/ር ዐቢይ ደስተኛ ነን፤ እናመሰግናለን፡፡
አሁን በድንበር አካባቢ የፀጥታና የትብብር ጉዳይ ምን ይመስላል?
ደቡብ ሱዳን ውስጥ ቀውስ በነበረ ጊዜ የተለያዩ ቡድኖች፣ በርካታ ህፃናትን ከኢትዮጵያ ጠልፈው ወስደው ነበር፡፡ ይሄ የሚያሳየው የድንበር አካባቢ የፀጥታ ሁኔታ አስተማማኝ አለመሆኑን ነው፡፡ የደቡብ ሱዳን መንግስት፣ ከተቃዋሚዎች ጋር ጦርነት ላይ ስለነበር ድንበሮችን መቆጣጠር አልቻለም። ኢትዮጵያም በዚያ ድንበር አካባቢ እንዲህ አይነት አስደንጋጭ ችግር ይፈጠራል ብላ አላሰበችም ነበር፤ ግን ተፈጠረ፡፡ ይህን ሁላችንም የምናስታውሰው ነው። አሁን ከረጅም ችግር በኋላ እኛም ወደ ሰላም የመጣን በመሆኑ፣ የድንበር አካባቢ ፀጥታ አስተማማኝ ይሆናል። ለዚህ ደግሞ ኢትዮጵያና ደቡብ ሱዳን ተባብረው በመስራት፣ ሰላምና ጉርብትናቸውን ያጠናክራሉ፤ ምንም የሚያጠራጥር አይደለም፡፡ መንገዶች ይከፈታሉ፤ የድንበር አካባቢ ንግድ ይጀመራል፡፡
ከኢትዮጵያ ጋር ያላችሁን ጉርብትና ይበልጥ ለማጠናከር መንገዶችንና የባቡር መስመሮችን የመዘርጋት እቅድ ይኖራል?
ይህንንም ለመስራት ስምምነት ተፈርሟል፡፡ ለምሳሌ የባቡር መስመርን በተመለከተ፣ ከጅቡቲ አዲስ አበባ፣ ከአዲስ አበባ ጁባ ለመዘርጋት ስምምነት ተፈርሟል፡፡ ፕሮጀክቱም ለአንድ የቻይና ኩባንያ ተሰጥቶ ፊርማ ተካሂዷል፡፡ የመኪና መንገድን በተመለከተ ሁለት ዋና ዋና መንገዶች አሉን። አንዱ መንገድ ከአዲስ አበባ ተነስቶ “ፓሎጅ” የተሰኘውና በብዛት ነዳጅ የሚመረትበት የደቡብ ሱዳን ቦታ ድረስ በቀጥታ የሚገባ ሲሆን ሁለተኛው ከጋምቤላ “ቦማ”ባለፈው ህፃናቱ ከተጠለፉበት ተነስቶ ጁባ የሚገባ ነው፡፡ በነገራችን ላይ የኢትዮጵያና የደቡብ ሱዳን ህዝቦች ወደዚያ ለመምጣትና ለመሄድ የግድ አውሮፕላን መጠቀም የለባቸውም፤ መኪና እየነዱ መግባት ይችላሉ፡፡ የድንበር አካባቢ ንግድና ቢዝነስ መስራት ይችላሉ፡፡ የደቡብ ሱዳን ህዝብ ብዙ ነዳጅ አለው። ኢትዮጵያም ነዳጅ ለመግዛት ሩቅ ሳትጓዝ፣ ከእኛ ማግኘት ትችላለች፡፡ እኛም ታላቁ የህዳሴ ግድብ ሲያልቅ የኤሌክትሪክ ኃይል ከኢትዮጵያ በቅርቡ መግዛትና መጠቀም እንችላለን። ብቻ ብዙ ነገሮች በትብብርና በጋራ ለመስራት እንዲሁም አገሮቻችንን ለማልማት የሚያስችሉን፣ የምንጠብቃቸው እድሎች አሉን፡፡ ይሄ በጣም የሚያስደስትና በተስፋ የሚሞላ ነገር ነው፡፡ የውጊያ ቦታ የነበሩትን ቀጠናዎች፣ የልማት ጣቢያዎች ማድረግ እንችላለን፡፡
አገራችሁ ቀውስ ውስጥ በነበረች ጊዜ በርካታ ዜጎች መሰደዳቸው ይታወቃል፡፡ ለመሆኑ ምን ያህል ይሆናሉ የተሰደዱት? ወደ አገራቸው ለመመለስ ምን ታቅዷል?
የአገሪቱን ቀውስ ተከትሎ የተፈናቀሉ በርካታ ቁጥር ያላቸው ዜጎች በጋምቤላ፣ በሀዋሳና እዚያው ጋምቤላ ውስጥ ፑኚዶ በተሰኙ ቦታዎች ይገኛሉ፡፡ እስካሁን ሪፖርቶች የሚያመለክቱት፤ ከ35 ሺህ በላይ ስደተኞች እንዳሉ ነው። የስደተኞቹ ሁኔታ … አገሪቱ ሰላም ስትሆን ወደ አገራቸው ስለሚመለሱ ይቀንሳል፤ እንደገና ቀውስ ሲነሳ ተመልሰው ስለሚሰደዱ ከፍ ይላል፡፡ እነሱን ወደ ቤታቸው በዘላቂነት ለመመለስ አገሪቱ በአስተማማኝ ሁኔታ ሰላም መሆን አለባት። አሁን ያንን ሰላም በእጃችን አስገብተናል፡፡ በአሁን ሰዓት ራሱ ጁባ ውስጥ ሰላም ሰፍኗል፡፡ የጥይት ጩኸት ከቆመና ሙሉ ለሙሉ ሰላም ከሆነ፣ በራሳቸው ጊዜም ወደ ቤታቸው ይመለሳሉ፡፡ እኛም የስደተኞች ማቋቋሚያ ፕሮጀክት አለን፤ ሁሉም ጥሩ ይሆናል፡፡
ደቡብ ሱዳን እንደ አገር እውቅና ካገኘችና የተባበሩት መንግስታት አባል አገር ከሆነች በኋላ ከሌላው ዓለም ጋር ያላት ግንኙነት ምን ይመስላል?
እኛ ከየትኛውም የአለም ህዝብ ጋር ችግር የለብንም። ቅድም ከነገርኩሽ ከሩቅ አገር እየመጡ ጣልቃ እየገቡ ከሚበጠብጡን በስተቀር፣ ሌላው ቀርቶ ከጎረቤቶቻችን ከየትኞቹም ጋር በሰላምና በፍቅር ነው የምንኖረው፡፡ ከሩቅ መጥተው ችግር እንፈታለን በሚል፣ የራሳቸውን ፍላጎት ለማስፈፀም የሚረብሹት ከቆሙልን፤ ከየትኛውም ጎረቤትም ሆነ የሌላ አለም አገራት ጋር ሰላማዊ ግንኙነት ነው ያለን፡፡ እርስ በእርሳችን የምንናቆርበት ጦርነትም ፍፃሜ አግኝቷል። በጣም ጥሩና የተረጋጋ አገርና ህዝብ ይኖረናል፤ እናድጋለን እንለማለን፡፡ አመሰግናለሁ፡፡   


     የኢትዮጵያ የግብር ስርአት ኋላ ቀር እንደመሆኑ መጠን ከቅርብ አስርተ አመታት ወዲህ የግብር ስርዐቱን ለማዘመን በተሻለ የግብር አሰባሰብና በዘመናዊ የካሽ ሬጅስተር ማሽን የታገዘ ቢሆንም፣ የውስጥ አደረጃጀቱ ግልጽነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት ባለመሆኑ፣ የግብር ስርዓቱ የጥቂት ግለሰቦችን ካዝና ሲሞላ እንደነበር ያደባባይ ምስጢር ነው፡፡  
ይህንኑ የምዝበራ ክፍተት ለመሙላትም መካከለኛና አነስተኛ ግብር ከፋዮች ላይ ተመጣጣኝ ያልሆነ ግብርና ታክስ በመጫን፣ “ክፈል አልችልም” በሚል እሰጥ አገባ፣ በየፋይናንስ ቢሮዎች ቅሬታ ሰሚ ጉባኤና በየፍርድ ቤቱ የሚጉላላው ግብር ከፋይ ቁጥር ቀላል የሚባል አይደለም፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ስለ ግብር አሰባሰብ በቅርቡ በፓርላማ ባደረጉት ንግግር፤ በሀገራችን ያሉ ወደ ሶስት ሺ የሚጠጉ ከፍተኛ ግብር ከፋዮች ግብራቸውን ባግባቡ ቢከፍሉ በቂ በመሆኑ ታች ወርደን አነስተኛ ግብር ከፋዮችን ባላስጨነቅን ነበር ብለዋል፡፡ ይሁን እንጅ ሁሉም ግብር ከፋዮች በየደረጃቸው የሚፈለግባቸውን ግብር የመክፈል አገራዊ ግዴታ እንዳለባቸው እሙን ነው፡፡
ሆኖም ግብር ከፋዮች በየበጀት አመቱ በሂሳብ መዝገብ አቅርበው፣ ከከፈሉት ግብር ውጭ “ገቢ አነሰ” በማለትና ዘመናዊ የሂሳብ አያያዝ ዘዴን በሚጻረር “የዴስክ ኦዲት ግኝት” በተባለ የውስጥ አሰራር ተገቢ ላልሆነ የግብር ጫና ከመዳረጋቸውም በላይ በየበጀት ዓመቱ የሚቀርበው የሂሳብ መዝገብ፣ በወቅቱ ባለመመርመሩና ለብዙ አመት በመወዘፉ ምክንያት ወደፊት በተገኘው አጋጣሚ ሲመረመር የሚገኘው የልዩነት ግብር ከተጠራቀመ የባንክ ወለድና መቀጫ ክፍያ ጋር ተዳምሮ፣ ግብር ከፋዩን እንደሚጎዳው ይታወቃል፡፡
ስለሆነም አሁን አገራችን በሰነቀችው የይቅርታ፣ የምህረትና በፍቅር የመደመር ጉዞ መሰረት የታክስ ስርአቱም ለተወሳሰበውና ለተወዘፈው የውሳኔ አሰጣጥ ችግር የምህረት አዋጅ አድርጎ፣ በአዲስ መልክ የአሰራር ስርአቱን ሊያዘመን ይገባል እላለሁ፡፡
ዳኘ ከአዲስ አበባ ፒያሳ