Administrator

Administrator

…ደግነትና ቅንነት ቆመው ቢሄዱ አስፋው ናቸው…”

በአሜሪካ  ዋሽንግተን ዲሲ በሚገኘው የጆርጅ ዋሽንግተን ዩኒቨርስቲ ሆስፒታል ህክምናውን ሲከታተል ቆይቶ ባለፈው ቅዳሜ ጥር 4 ቀን 2016 ዓ.ም ከሌሊቱ 9 ሰዓት ላይ ያረፈው የኢቢኤስ ቴሌቪዥን የመዝናኛ ፕሮግራም አዘጋጁና አቅራቢው አስፋው መሸሻ አስከሬን ነገ ወደ ኢትዮጵያ እንደሚገባ ተነግሯል። እዚህ አዲስ አበባ የቀብር ሥነ-ስርዓቱን የሚያስፈጽም ኮሚቴ ተዋቅሮ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑ የተጠቆመ ሲሆን፤ የቀብር ሥነ-ስርዓቱ ከነገ ወዲያ ሰኞ እንደሚከናወን ተገልጿል።
ተወዳጁ የሬዲዮና ቴሌቪዥን ፕሮግራም አዘጋጁና አቅራቢው አስፋው መሸሻ ከኢቢኤስ የቴሌቪዥን ጣቢያ አስቀድሞ በኤፍኤም አዲስ 97.1 “አይሬ”  የሙዚቃ ፕሮግራሙ ዕውቅናና ተወዳጅነትን ማትረፉን ይታወቃል። ከዚያም በኢቢኤስ ይተላለፍ ከነበረው “ኑሮ በአሜሪካ” እስከ “እሁድን በኢቢኤስ” መሰናዶ ድረስ በብዙዎች ዘንድ ተወዳጅነትን አትርፏል።
አስፋው መሸሻን በሥራ ባልደረባነትና በጓደኝነት ለ20 ዓመታት ገደማ የሚያውቀው በአሜሪካ የኢቢኤስ ባልደረባ ጋዜጠኛ አበበ ፈለቀ ለቪኦኤ በሰጠው ምስክርነት፤ “…ደግነትና ቀናነት በእግር ቆመው ቢሄዱ አስፋው ናቸው…” ብሏል።
አስፋው በአሜሪካ  በህክምና ላይ ሳለ ያስተዋልኩት የህዝብ ድጋፍና ፍቅር ከአዕምሮዬ በላይ ነው ሲል የተናገረው ጋዜጠኛ አበበ ፈለቀ፤ “ሆስፒታል መጥቶ ልጠይቅህ ላስታምህ ከሚለው ባሻገር… በፀሎትም በገንዘብም…. በስልክም በመንፈስም… ሁሉም ሰው አብሮት ነው የቆመው” ብሏል። “አስፋው በህዝብ ፍቅር ታጅቦ ነው የኖረውም ያለፈውም” ሲልም ምስክርነቱን ሰጥቷል።
ካለፈው ረቡዕ ጀምሮ በአሜሪካ የስንብትና የሽኝት ፕሮግራም እንደሚደረግለት ለሬዲዮ ጣቢያው የገለፀው አበበ ፈለቀ፤  ጥር 13 ቀን 2016 ዓ.ም የአስፋው መሸሻ አስክሬን ወደ ኢትዮጵያ እንደሚላክ ጠቁሟል።
ከአባቱ አቶ መሸሻ አስፋውና ከእናቱ ወ/ሮ ዘነበወርቅ አሻግሬ ሃምሌ 19 ቀን 1959 ዓ.ም የተወለደው አስፋው መሸሻ፤ የአንድ ልጅ አባት ነበር።የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል፣ በአንጋፋው የሬዲዮና ቴሌቪዥን ፕሮግራም አዘጋጅና አቅራቢ አስፋው መሸሻ ህልፈት የተሰማውን ጥልቅ ሃዘን እየገለፀ፤ ለቤተሰቦቹ፣ ለስራ  ባልደረቦቹና ለወዳጆቹ ሁሉ መጽናናትን ይመኛል። ፈጣሪ ነፍሱን በአፀደ ገነት ያኑርለት።

ም/ቤቱ ሁለቱ አገራት አለመግባባታቸውን በንግግር እንዲፈቱ መክሯል
የሶማሊያ ባለሥልጣናት ጦርነት ቀስቃሽ ዛቻዎችን መሰንዘር ቀጥለዋል

የአፍሪካ ህብረት የሰላምና የፀጥታ ምክር ቤት ባለፈው ረቡዕ ጥር 8 ቀን 2016 ዓ.ም በኢትዮጵያና በሶማሊያ መካከል የተፈጠረውን ውጥረት አስመልክቶ ውይይት ያደረገ ሲሆን፤ የውጭ  ሃይሎች በሁለቱ አገራት መካከል ጣልቃ ከመግባት እንዲቆጠቡ አሳስቧል። ምክር ቤቱ የቀድሞው የናይጄሪያ ፕሬዚዳንት ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ ውጥረቱን ለማርገብ ጣልቃ ገብተው ውይይት እንዲያስጀምሩ ህብረቱን ጠይቋል።ሶማሊያ፤ በቅርቡ ኢትዮጵያ ከሶማሊላንድ ጋር የደረሰችው ስምምነት ሉአላዊነቷን የሚጥስ መሆኑን በመግለፅ ውድቅ ያደረገችው ሲሆን፤ አሁንም ድረስ በኢትዮጵያ ላይ ዛቻና ማስጠንቀቂያ በይፋ መሰንዘሯን ቀጥላለች።
ኢትዮጵያና ሶማሊላንድ በቅርቡ በተፈራረሙት የመግባቢያ ሰነድ መሰረት፤ ሶማሊላንድ ለኢትዮጵያ የባህር በሯን የምታከራይ ሲሆን፤ ስምምነቱ ወታደራዊ ትብብርንም ያቀፈ ነው ተብሏል። ሶማሊላንድም በምላሹ ከአትራፊው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አክስስዮን እንደምታገኝ ተነግሯል። ኢትዮጵያ ወደፊት ለሶማሊላንድ የአገርነት ዕውቅናም ልትሰጥ እንደምትችል ተሰምቷል።የአፍሪካ ህብረት የሰላምና የፀጥታ ምክር ቤት ባለፈው ረቡዕ ባካሄደው ስብሰባው፤ ኢትዮጵያም ሆነች ሶማሊያ በህብረቱና በዓለማቀፉ ህግ መሰረት ውጥረቱን እንዲያረግቡ ጥሪ አቅርቧል።
ምክር ቤቱ በዚህ ስብሰባው በህብረቱ የኢትዮጵያ መንግሥት ተወካይ አምባሳደር አየለ ሊሬና የሶማሊያው አቻቸው አምባሳደር አብዱላሊ ዋርፋ አስተያየትን አድምጧል ተብሏል። ምክር ቤቱ ከስብሰባው በኋላ ባወጣው መግለጫም፤ የውጭ ሃይሎች በሁለቱ የህብረቱ አባል አገራት መካከል ጣልቃ ከመግባት እንዲቆጠቡም አሳስቧል።
ሁለቱ አገራት ያላቸውን የጎረቤትነት መንፈስ ከሚያውክ ተጨማሪ ተግባር አንዲቆጠቡ ያሳሰበው ምክር ቤቱ፤ አለመግባባታቸውን በንግግር እንዲፈቱም መክሯል።ኢትዮጵያ ከሶማላንድ ጋር የደረሰችውን ስምምነት ተከትሎ፣ በኢትዮጵያና በሶማሊያ መካከል የተፈጠረውን ውጥረት ለማብረድ በየአቅጣጫው የተለያዩ ጥረቶች እየተደረጉ ቢሆንም፤ ከሶማሊያ መንግስት ከፍተኛ አመራሮች በኩል ጦርነት ቀስቃሽ የሆኑ ጠንካራ አስተያየቶችና ዛቻዎች እየተሰነዘሩ ይገኛሉ።የሶማሊያ ፕሬዚዳንት ሐሰን ሼክ ሞሃመድ ባለፈው አርብ ጥር 3 ቀን 2016 ዓ.ም በአንድ መስጊድ ውስጥ ከተካሄደ የጸሎት ሥነ-ስርዓት በኋላ ባደረጉት ንግግር፤ “ከዚህ ቀደም የወረራ ሙከራቸውን ተከላክለናል፤ ከዚህ ቀደም አሸንፈናቸዋል፤ አሁንም እናሸንፋቸዋለን” ብለዋል።
የሶማሊያ ጠ/ሚኒስትር ሐምዛ አብዲ በበኩላቸው፤ ከኢትዮጵያ ጋር ጦርነት ውስጥ ለመግባት ዝግጁ መሆናቸውን ባለፈው ቅዳሜ መናገራቸው ተዘግቧል።
“… ወደ ሶማሊያ ግዛት አንድ ኢንች ለመግባት ቢሞክሩ፤ አስከሬኖችን ይዘው ወደ አገራቸው ይመለሳሉ።” ብለዋል፤ ጠ/ሚኒስትሩ።በሁለቱ አገራት መካከል የተፈጠረው ውዝግብና ውጥረት ክፉኛ ያሳሰበው የአፍሪካ ህብረት የሰላምና የጸጥታ ም/ቤት ባለፈው  ረቡዕ ባደረገው ስብሰባ፤ የውጭ ሃይሎች በሁለቱ አገራት መካከል ጣልቃ ከመግባት እንዲቆጠቡ አሳስቦ፣ የቀድሞው የናይጄሪያ ፕሬዚዳንት ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ ውጥረቱን ለማርገብ ንግግር እንዲያስጀምሩ ለአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ጥያቄ አቅርቧል።

ከዕለታት አንድ ቀን በአንድ መንደር በየዕለቱ የሚፈጠር አንድ ችግር ነበር፡፡ የችግሩ መንስዔ በየማታው እየሰከረ የሚመጣ አንድ ወንደላጤ መኖሩ ነበር፡፡
የሚፈጥረው ዋንኛው ችግር ልክ እሱ ሲመጣ የመንደሩ ውሾች መጮህ መጀመራቸውን ሲሆን “በእኔ ላይ በእኔ ላይ ነው የምትጮሁት? ማን መሰልኳችሁ? ሁሌ ስመጣ ቅንጣቢ ስጋ የምሰጣችሁ እኮ ነኝ? በዓመት በዓልማ ማነው አስቦ ስጋ ይዞላችሁ የሚመጣው? ልክ እንደ ዛሬ ማለቴ ነው!?”
ውሾች መጮሃቸውን አላቋረጡም፡፡  ያ ሰካራምም እንደ ወትሮው ድንጋይ ይለቃቅምና መወርወር ይጀምራል፡፡ ይስታቸዋል - በስካር ዐይንና በስካር እጁ በመሆኑ፡፡ በአካባቢው ያለውን የብረትም የቆርቆሮም በር ያናጋዋል፡፡
የብረትና የቆርቆሮውን በር እንዲሁም ውሾቹን ያልፍና መንገዱን ይቀጥላል፡፡ ሌላ ብረት በር ፊት ለፊት ይደርሳል፡፡ ሌሎች ውሾችም ብቅ ብቅ ይሉና ይጮሁበታል፡፡
“ኧረ በፋሲካ ምድር አታሳብዱኝ?” ይልና ድንጋዩን ሰብስቦ መወርወሩን ይቀጥላል፡፡ ይስታል፡፡ የሌሎቹን በር ይመታል፡፡ እንዲህ እንዲያ እየሆነ ለወራት ሰፈር ሲበጠብጥ  ይከርማል፡፡ የሰፈሩ ሰው በዚህ ሰው ጉዳይ ላይ መመካከር ጀመረ፡፡
“እንደው የዚህን ሰካራም ነገር ምን ብናደርግ ይሻላል?”
አንዱ፡-
“በራችን የተሰበረብን ሰዎች እንሰብሰብ”
ሁለተኛው፡-
“ምን ልንሆን?!”
ሦስተኛው፡-
“እንመካከርና መፍትሄ እንድናመጣ ነዋ?!”
አራተኛው፡-
“ይሄ በጣም መልካም ሀሳብ ነው! የሰፈሩ ሰው ይንቀሳቀስ፡፡ ይምከርና መላ ያብጅ እንጂ እስከመቼ አንድ ሰው ተሸክመን እንዘልቃለን? ላንዴም ለሁሌም ዘላቂ ዘዴ እንዘይድ!”
ሁሉም በሀሳቡ ተስማሙ፡፡
አንድ እሁድ ማለዳ የመንደሩ አዛውንቶች እንዲያገኙት ቀጠሮ ተያዘ፡፡
ተገኘላቸው፡፡
የፋሲካ እለት  ጠዋት፡፡
እንዲህ አሉ የአዛውንቶቹ ተወካይ፡-
“አየህ አንተ የመንደራችን ህዝብ ውድ ወንድም ነህ፤ ስለዚህ ቀረብ ብለን ልናወያይህ ነው አመጣጣችን”
እሱም፡-
“ስለምን ጉዳይ ልታማክሩኝ አሰባችሁ?”
ሽማግሌዎቹ፡-
“ወንድማችን መቼም መጠጥ ጎጂ መሆኑን ማንም አያጣውም፡፡ አንተም ጎጂነቱን አትስተውም!”
እሱም፡-
“እንዴታ! እንዴት እስተዋለሁ?”
ሽማግሌዎቹ፡-  “አየህ አምሽተህ ስትመጣ ከውሾች ጋር ትጣላለህ፤ ድንጋይ ትወረውራለህ፡፡ የሰው በር ትመታለህ፡፡ ይሄ ሁሉ የመነጨው አምሽተህ በመምጣትህ ምክንያት ነው፡፡ ስለዚህ ወንድማችን ሆይ እባክህ አታምሽ!”
እሱም፡-
“ውይ አባቶቼ እንዲያው በከንቱ አደከምኳችሁ! አሁንማ ማምሸት ትቼ! አሁንማ ተመስገን ነው፡፡ እያነጋሁ ነው የምገባው!”
***
ኢትዮጵያ ትንሳኤ ያስፈልጋታል፡፡ የዲሞክራሲ መስዋዕትነቷ አብቅቶ የተባ ትንሳኤ ያሻታል፡፡ የወገናዊነት በደሏ ይሻር ዘንድ ትንሳኤ ያስፈልጋታል፡፡ የፍትህ እጦት መከራዋ ይወገድ ዘንድ ትንሳኤን ትሻለች፡፡ በእድሜዋ ያልገጠማትን ዓይነት የመፈናቀል አደጋዋ ለአንዴም ለሁሌም ይታገድ ዘንድ “ኢትዮጵያ ታበፅዕ እደዊሃ ሀበ እግዚአብሄር” መባሉ ዛሬም መኖር አለበት (ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሄር ትዘረጋለች እንደማለት ነው)፡፡ ፍትህ ርትህ ያልተጓደለባት፣ ለአንዱ እናት ለአንዱ እንጀራ እናት እንዳትሆን፣ ልጆቿ እንዲታገሉላት ትፀልያለች፡፡ የትምህርት ስርዓቷ ደክሞ ከሚያንቀላፋበት ቀና ብሎ ወደ ጥንቱ ጠንካራ ንቃቱ ይመለስ ዘንድ አማልከቱን ትማለዳለች፡፡ የህዝብ ጤነኝነት የአገር ጤና ነውና የጤናም ትንሳኤ ያሻታል፡፡ ከለማበት የተጋባበት እንዲሉ፣ የጎረቤት አገሮች በሽታ እንዳይተላለፍባትና ድንበሯ ይከበር ዘንድ ህዝቧ አንድነቱን እንዲጠብቅ፣ የውስጥ ጥንካሬው በይዘትም በቅርፅም እንዲታነፅ አራሽ፣ ቀዳሽ፣ ተኳሽ ልጆቿ እንዲበረቱ አምላኳን ትማጠናለች፡፡  የህዝቦቿ ልቦና በቅንነትና በፍቅር እንዲከፈት ፀሎቷን ማሰማት አለባት፡፡ ከሚያወሩ አፎች ይልቅ የሚሰሩ እጆች መድህኖቿ መሆናቸውን ልጆቿ  ማወቅ አለባቸው፡፡
ኢትዮጵያ በመታገል እንጂ በእድል እንደማትለማ መገንዘብ ግዷ ነው፡፡
ዛሬም ከገሞራው ጋር
“..ነገሩ አልሆን ብሎ ሁኔታው ሲጠጥር
ጠጣሩ እንዲላላ የላላውን ወጥር”
…ማለት አለባት፡፡
መሪዎች የህዝብ የልብ ትርታ  ማዳመጥ አለባቸው፡፡ ፖለቲካዊ ቅሬታውንና ኢኮኖሚያዊ ብሶቱን ከልብ ማዳመጥ ዋና ነገራቸው ነው፡፡ ህዝብም ጉዳዩን ሁሉ ለመሪዎች ጥሎ እጆቹን አጣጥፎ መቀመጥ የለበትም፡፡ አገር “ቀኗ ሲደርስ ትቀናለች” የምትባል የምኞት አስኳል አይደለችም፡፡ “መንገዶች ሁሉ ወደ ልማት ያመራሉ” ብሎ መመኘት በስራ ካልታገዘ ምኞት ብቻ ነው፡፡ ዱሮ ስለ ትግል ሲወራ “ጉዟችን ረዥም ትግላችን መራራ ነው” ይባል ነበር፡፡ ይሄን ሲሰብክ የቆየ ካድሬ ቀና ጎድሎበት ታሰረ፡፡ መፈክሩን ፈተሸና፤
“ይሄ አግባብ አይደለም፡፡ መራራ ከሆነ አጠር ይበል፣ ረዥም ከሆነ ደግሞ ጣፈጥ ይበል እንጂ መራራም ረዥምም ማድረግ በጭራሽ በጎ አካሄድ አይደለም!” አለ አሉ፡፡
ጊዜ የማይለውጠው ነገር የለም፡፡ ለጊዜ ጊዜ መስጠት ብቻ ነው የሚጠበቅብን፡፡ ምናልባት ከደራሲ ከበደ ሚካኤል ጋር
“ለሁሉም ጊዜ አለው ብሏል ሰለሞን
እጠይቀው ነበር በተገናኘን
ሞት ራሱ እሚሞት ምን ጊዜ እንደሆነ”
…ማለትም ያባት ነው፡፡
 ከዚህ ቀደም፤
“እናትና አባቴን በጊዜ ቀብሬ
መንግሥት እጦራለሁ አንጀቴን አሥሬ”
…. እንል የነበረውን ቀይረን ለውጡን እንዴት እናግዝ? የሚለውን አቅጣጫ ማሰብ አንድ መላ ነው፡፡
መልካም የጥምቀት በዓል ይሁንልን!!

“TX Cargo Chassis” ዘመናዊ  የጭነት መኪና ለመጀመሪያ ጊዜ ለኢትዮጵያ ገበያ ቀረበ

በተሽከርካሪው ኢንዱስትሪ የሚታወቁት ሲኖትራክ ኢንተርናሽናልና ሃንሰም ግሩፕ፣ እጅግ ዘመናዊና የላቀ አቅም ያለው ነው ያሉትን “TX Cargo Chassis” የተሰኘ አዲስ የጭነት መኪና ለመጀመሪያ ጊዜ ለኢትዮጵያ ገበያ ማቅረባቸውን አስታወቁ፡፡

ሲኖትራክ ኢንተርናሽናልና ሃንሰም ግሩፕ፣ ይህን ያስታወቁት በዛሬው ዕለት ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በሂልተን ሆቴል በተዘጋጀ ሥነሥርዓት ላይ ነው፡፡

ኩባንያዎቹ ለአገሪቱም ሆነ በተለያየ ንግድ ላይ ለተሰማሩ ዜጎች ይበጃል ያሉት ይኸው አዲስ የጭነት ተሽከርካሪ፤ ፍጹም አዲስ ግብአቶችን አካትቶ፣ ነገር ግን ለተጠቃሚው በቀላሉ እንዲመች ተደርጎ የተመረተ መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡

“TX Cargo Chassis የተነደፈው ልዩና የተቀላጠፈ አሰራርን የሚያግዙ ግብአቶችን በማካተት፣ ብቃትን በማሳደግ እንዲሁም ጊዜንና የጥገና ወጪን በሚቀንስ መልኩ ነው” ብለዋል፤ ኩባንያዎቹ በሰጡት መግለጫ፡፡

ተሽከርካሪው ባለሦስት ድርብ፣ ሙሉ ለሙሉ ብረት የሆነ ጠንካራ መከላከያ የተገጠመለት ሲሆን፤ ይህም መኪናው በማንኛውም ጊዜና በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ለሚደረጉ እንቅስቃሴዎች እንዳይበገር ከማድረጉም በላይ የጥገና ወጪን የሚቀንስና የአገልግሎት ዘመኑን የሚያረዝም ነው ተብሏል፡፡

ከ2001 እስከ 2015 ዓ.ም ባሉት ጊዜያት ሲኖትራክ ኢንተርናሽናልና አጋሩ ሃንሰም ግሩፕ በጋራ ከ80ሺ በላይ ተሽከርካሪዎችን ከመሸጣቸውም በላይ ከ400 ሺ በላይ ተዛማጅ  የሥራ ዕድሎችን በሃገር ውስጥ  መፍጠራቸውን በመግለጫቸው ጠቁመዋል፡፡

የደራሲ ቴዎድሮስ መብራቱ "ንሥር እና ምስር"ሁለተኛ ዕትም መጽሐፍ ከሰሞኑ ለአንባቢያን ደርሷል።ደራሲው ሁለተኛው ዕትም መጽሐፉ ተሻሽሎ እንደቀረበም ገልጿል።መጽሐፉን በተለያዩ የመጻሕፍት መደብሮች ታገኛላችሁ።

"ትዝታሽን ለእኔ ትዝታዬን ለአንቺ" መጽሐፍ
ደራሲ እሱባለው አበራ "ፀሐይ ከጨለማዬ ምን አለሽ?" የተሰኘ ሁለተኛ መጽሐፉን ትላንት ረቡዕ ጥር 8 2016 ዓ.ም ለአንባቢያን አቅርቧል።
መጽሐፉን ጃፍርን ጨምሮ በተለያዩ የመጻሕፍት መደብሮች ታገኛላችሁ ተብላችኋል።

መጽሐፉ በዋናነት የኢትዮጵያ ችግሮች፣ መንሥዔዎች እና የመፍትሔ ሀሳቦች ላይ ትኩረቱን ያደርጋል ተብሏል። በአምስት መቶ ብር  ለአንባቢያን ቀርቧል።

 ዮናስ ታረቀኝ ይባላል፡፡ በጀርመን ባህል ማዕከል የቤተ መፃህፍትና የመረጃ ሃላፊ ነው፡፡ ከአስር በላይ የተለያዩ መጻሕፍትን ከጀርመንኛና ከእንግሊዝኛ በመተርጎም ለአንባቢ ማድረሱን ይናገራል፡፡ በቅርቡ ለንባብ በበቃውና በጀርመን ባህል ተቋም ሙሉ ድጋፍ በታተመው “ሠላሳዎቹ” የተሰኘ የአጫጭር ልብወለዶች መድበል ላይ ከሃሳብ ማመንጨት እስከ ማስተባበር ድረስ ተሳትፏል፡፡ በአጭሩ የፕሮጀክቱ መሪ ነበር፡፡ ለዮናስ ታረቀኝ “ሠላሳዎቹ” በተሰኘው የአጫጭር ልብወለዶች መድበልዙሪያ አንዳንድ ጥያቄዎችን ላቀርብለት እንደምፈልግ ስነግረው ምንም ሳያቅማማና ለደቂቃ ማሰብ ሳያስፈልገው ፈጣን ምላሹንበመስጠቱ ምስጋና ይገባዋል፡፡ ከዚያም በላይ ግን ሥራዎቻቸው በመፅሐፉ የተካተተላቸው ደራስያንም የመጠየቅና ሃሳባቸውንየመግለጽ እድል ያገኙ ዘንድ ያቀረበልኝ ሃሳብ አስደምሞኛል፡፡ እውነቱንም ነው፡፡ በዚህ መሰረት በቀጣይ ሳምንታት ከጥቂቶቹጋር ቆይታ ይኖረናል ማለት ነው፡፡ ለዛሬ ግን ከደራሲና ተርጓሚ ዮናስ ታረቀኝ ጋር በ“ሰላሳዎች” መድበል ዙሪያ ያደረግነውን አጭር ቃለ ምልልስ እንዲህ አጠናቅረነዋል፡፡



           “ሠላሳዎቹ” የተሰኘውን የአጫጭር ልብወለዶች መድበል የማሳተም ሃሳቡ እንዴት ተጠነሰሰ? መቼና በማን ?
የጀርመን ባህል ማዕከል ባለፉት  አስርት ዓመታት በሀገራችን ውስጥ የንባብ ባህል እንዲዳብር የተለያዩ ሙከራዎችን ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ ጥቂቶችን ለመጥቀስ ያህል፡- ወርሃዊ የመጽሐፍ ውይይቶች (በአካልም በኦንላይንም)፣ ሀገር አቀፍ የንባብ ፌስቲቫሎች (አዲስ አበባ ታንብብ፣ ኢትዮጵያ ታንብብ)፣ የተረት ሳምንት በተለያዩ ትምህርት ቤቶች ውስጥ፣ በየቤተ መጻሕፍቱ ከደራሲያን ጋር  የሚደረግ የንባብና የልምድ ማካፈል (ንባብን ባህላችን እናድርግ በሚል መርህ ስር)፣ በንባብ ለህይወት የመጽሐፍ አውደ ርዕይ ላይ በመሳተፍ ደራሲያንን ከታዳሚያን ጋር የማገናኘትና የማስፈረም እንዲሁም በተለያዩ ስነ ጽሑፋዊ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ውይይት የማካሄድ መርሃ ግብሮችን ማከናወን፣ የጀርመን ደራሲያንን ስራ በንባብ፣ በውይይት እንዲሁም ስራዎቹ እንዲታተሙ በማድረግ ማስተዋወቅ የመሳሰሉት ይገኛሉ። “ሠላሳዎቹ” የእነዚህ የተለያዩ እንቅስቃሴዎች ውጤት ነው።  ገፊ ምክንያቶቹ፣ አሁን ሀገራችን ውስጥ ባለው ሁኔታ መጽሐፍ ማሳተም እጅግ ፈታኝ መሆኑ፤ የሀገራችን ወጣት ጸሐፍት የህትመት ብርሃን እንዲያገኙላቸው የሚፈልጓቸው ርዕሰ ጉዳዮች ምንድናቸው? ምን ያሳስባቸዋል? ስለምን መጻፍ ይፈልጋሉ? ይህንንስ እንዴት ባለ ስነ ጽሑፋዊ ለዛ ያቀርቡታል? የሚሉ ጥያቄዎች፤ እንዲሁም እጅግ በጣም በጥቂቱ ቢሆንም የኢትዮጵያዊ ወጣት ስራዎችን ቢያንስ ወደ ጀርመንኛ አፍ መልሶ ለጀርመን ማህበረሰብ የማቅረብ ፍላጎቶች ናቸው። መነሻ ሃሳቡን እኔ ያነሳሁት ቢሆንም እንዲዳብር በማድረግ የተሳተፉ ወዳጆቼ ብዙ ናቸው። የጀርመን ባህል ተቋም ደሞ ተቀብሎትና አምኖበት፣ በጀት መድቦ የተካሄደ ነው።    
ጸሃፊዎቹ ካልተሳሳትኩ አዳዲሶች ናቸው--- በአጭር ልብወለድ ሥራዎቻቸው  የምናውቃቸው ጸሃፍት አልተሳተፉም ብዬ ነው? ሆን ብላችሁነ ነው?
ጽሑፎቹን ለመሰብሰብ የታሰበው በውድድር መልክ ስለነበር፣ መስፈርቶች መውጣት ነበረባቸው። ስለዚህ አንዱ ያደረግነው የዕድሜ ገደብ ማስቀመጥ ነው። ይኸውም ከ18 እስከ 35 ዓመት የሚል ነበር፤ ከ-እሰከው ትንሽ ሰፋ ያለ ቢሆንም፡፡ ስለዚህ ምንም አንኳን ጥቂት ከዚህ በፊት የታተሙ ስራዎች የነበሯቸው ጸሐፍት ቢኖሩም፣ አብዛኛዎቹ አዳዲሶች ናቸው። እድሉን መስጠት የፈለግነውም በተቻለ መጠን ለጀማሪና አዳዲስ ጸሐፍት ነበር። ዋናው ትኩረታችን የነበረው ግን ያቀረቡት ስራ አዲስነት ላይ ነበር።   
ልምድ ከሌላቸውና ከጀማሪ  አዳዲስ ጸሐፍት ለህትመት ብቁ የሆኑ  ታሪኮችን  በቀላሉ ማግኘት አያስቸግርም ?  አድካሚስ አይሆንም ?
የማይታወቅና ልምድ የሌለው ጸሐፊ ለህትመት የሚበቃ ምርጥ ስራ ሊያቀርብ አይችልም የሚል እምነት የለኝም። ብዙ “ዋው” ያስባሉን፤ እጃችንን አፋችን ላይ ያስጫኑን፣ ከዚህ በፊት የማናውቃቸው ጸሐፍት ስራዎችን አንብበናል። እነዚህን ስራዎች ያቀረቡልን ግን ሳይደክሙ አልነበረም። ልምድ ደሞ ያለ ድካም አይገኝም። ወደ እኛ ጉዳይ ስመጣም ተመሳሳይ ነው።  መጀመሪያ እድሉን መስጠት ነው የፈለግነው፣ በራሳቸው ተማምነው ስራዎቻቸውን የላኩትን በሙሉ አድንቀን ነው የተቀበልነው። በውድድሩ መስፈርት (ለምሳሌ የተመጠነ የገፅ ብዛት) እና ሌሎችም፣ በዳኞች በተቀመጠ ስነ ጽሑፋዊ መመዘኛ መሰረት ከቀረቡልን 103 አጫጭር ልቦለድ ታሪኮች ውስጥ በዳኞች መካከል ከተካሄደ የከረረ ውይይት በኋላ 30 አጫጭር ልቦለዶችን ብቻ ማውጣት፣ ማድከሙ አይቀሬ ነው። የተመረጡት 30 ስራዎች እንዳሉ አይደለም ለህትመት የበቁት። ለጸሐፍቱ ከስራዎቻቸው በመነሳት ጥሩ እና ጥሩ ያልሆኑ ጎኖች የተዳሰሱበት፣ መሻሻል የሚኖሩባቸው ነገሮች የተመለከቱበት፣ መሰረታዊ የስነ ጽሑፍ ጉዳዮች የተጠቆሙበትና ልምዶች የተካፈሉበት፣ የሁለት ቀናት ስልጠና ተሰጥቷል። በመቀጠል ፀሐፍቱ ከተሰጣቸው ስልጠና በመነሳት ጽሑፎቻቸውን መልሰው እንዲያዩ፣ እንዲያሻሸሉ፣ እንዲጨምሩ እንዲቀንሱ ሰፊ እድል እንዲሰጣቸው ተደርጓል። በመጨረሻም ከአርታኢያቸው ጋር በመሆን ለሕትመት ብቁ እስኪሆን ድረስ ተግተዋል። አርታኢውም በጣም ለፍቷል። ጥያቄህ አያደክምም ወይ አልነበር? ቀላል ያደከማል!
ታሪኮቹን ለማሰባሰብ ምን ያህል ጊዜ ፈጀባችሁ? በማሰባሰብ ሂደቱ የገጠሟችሁ ተግዳሮቶች ምን ነበሩ?
በትክክል ካስታወስኩ ወደ ሁለት ወር ገደማ የወሰደ ይመስለኛል። የሰበሰብነው በኢሚይል እንዲላክ በማድረግ ስለነበር፣ ብዙ ተግዳሮት አልገጠመንም። አልፎ አልፎ ግን መስፈርቱን የማያሟሉ ጽሑፎችና መስፈሩትን የማያሟሉ ጸሐፍት ያጋጥሙን ነበር።
የተለያዩ ጸሃፍት የፈጠራ ሥራዎች በጋራ መውጣታቸው ፋይዳቸው ምንድን ነው?
አንዱ እንደ ቡፌ የተለያየ ጣዕም መፍጠር መቻላቸው ነው። ብዙም ባይሆን ከአዲስ አበባ ውጪ የሚኖሩ ጸሐፍትም የተካተቱበት ነው። ይህ በራሱ የሚሰጠው ነገር ያለ ይመስለኛል። ቀጥታ ከዚህ ጋር መያያዝ ባይኖርበትም፣ በጸሐፍቱ መካከል መተዋወቅና ግንኙነት መፍጠር መቻሉም መልካም ነው ብዬ አስባለሁ። ምናልባት የ“ሠላሳዎቹ” መድበል የህትመት ዋጋ በጀርመን ባህል ተቋም በመሸፈኑ እንጂ፣ አሁን ባለው የህትመት ዋጋ መናር የተለያዩ ጸሐፍት ዋጋውን እየተጋሩ፣ በጋራ ስራዎቻቸውን ማውጣት ቢችሉ ፋይዳ ይኖረዋል ብዬ አስባለሁ።  
እስቲ  “በሠላሳዎቹ” የአጫጭር ልቦለዶች መድበል ውስጥ የተካተቱት ታሪኮች ምን እንደሚመስሉ በአጭሩ ጠቅልለህ ንገረን ?
እዚህ ላይ አርታኢው ቴዎድሮስ አጥላው በመጽሐፉ ላይ በመግቢያነት ካሰፈረው ጽሑፍ በላይ ሊያሳይልኝ የሚችል ስለማይኖር እሱኑ እንዳለ ብጠቅስ  ይሻላል።   
‘’በዚህ ሠላሳዎቹ ባልነው ስብስብ ከተካተቱት ሥራዎች አብዛኞቹ የደራሲዎቹን ወይም ድርሰቶቹ የተጻፉበትን ዘመን መንፈስ የሚወክሉ ናቸው። ደራሲዎቹ በጦርነት፣ በጥላቻ፣ ከሥር በመነቀል፣ በመካካድ፣ በአደጋዎች፣ በጭካኔ ድርጊቶች፣ በምንትነት መቃወስና በመሳሰሉት ነባራዊ ሁኔታዎች ምክንያት ከተፈጠረው የወል ድባቴ፣ የወል ትሮማ ያመለጡ አይመስሉም። ፊት ለፊት ባይኾንም በሥራዎቻቸው እነዚህን ለመግለጥ ወይም ለማምለጥ የሞከሩም ይመስላሉ። ለሕትመት በመረጥናቸው ሠላሳዎቹም ኾነ በተቀሩት ታሪኮች ውስጥ ሞት፣ የመኪና አደጋ፣ መካካድ፣ መወስለት፣ ድህነት፣ ኀዘን ጎልተው የሚሰሙ ድምጾች ናቸው። ከሁልዮ ኮርታዛር ዝነኛ አገላለጽ ብንዋስ፤ እነዚህ ሠላሳዎቹ የዚህን ዘመን መንፈስ በየራሳቸው መቃን ቀንብበው ያስቀሩ ሠላሳ “ፎቶግራፎች” ሲኾኑ፣ መድበሉ ደግሞ ጥየቃ ለመጣው አንባቢ እንግዳ የቀረበ አልበም ነው። (እንግዳው ፎቶዎቹ መሐል ራሱን መፈለጉ፣ አንዳንዴም ማግኘቱ አይቀርም።
በስልት ረገድ፣ ከተረኮቹ አንዳንዶቹ ለግል ማስታወሻነት የቀረበ አጻጻፍ አላቸው።የስሜትና የሐሳብ ጥልቀቶቻቸው ከምናብ የተፈጠሩ/የተቀመሩ ሳይኾን በአብዛኛው ከጸሐፊው/ተመክሮ የተቀዱ ያስመስሏቸዋል። ደግሞ አሉላችሁ፡-  በሥነ ልቡና እና በሥነ አእምሯዊ ሰብአዊ ጣጣዎች ላይ የተመሠረቱ፤ስለዚህም በይነዲሲፕሊናዊ ንባብን በተለይም ሳይኮአናሊሲስን የሚጋብዙ። ከጽንሰ ሐሳብ ለመዛመድ እንኳን ባይጻፉ፤ ግጭቶቻቸው፣ ጭብጦቻቸው፣የገጸባሕርያታቸው ጠባያትና ድርጊያዎቻቸው የሥነጽሑፍንና የሌሎች ሙያዎችን ጽንሰ ሐሳቦች በመፈከሪያነት የሚጣሩም አሉባቸው። ኢምክኑያዊ ፍርሓት፣ የአእምሮ ጤና እክል፣ ድባቴ፣ መርሳትና መዘንጋት፣ በራስ እጅ የማለፍ ግፊት፣ ኤዲፐሳዊ ምስቅልቅል፣… በአርእስተ ጉዳይነት ገንነውባቸው የሳይኮሎጂና የሳይካትሪ ሙያዎችን በማናበቢያነት ይጋብዛሉ። ‘’
እስቲ ታሪኮቹን ስታሰባስቡ ከጠየቃችኋቸው መስፈርቶች ሦስቱን ብቻ ጥቀስልኝ.....?
አንዱ እድሜ ነው፤ ቀደም ብዬ ጠቅሼዋለሁ። ሌላው የገፅ መጠኑ ከአምስት ያላነሰ፣ ከአስር ያልበለጠ የሚለው ነው። አንድ ሰው ለውድድር ማቅረብ የሚችለው አንድ ስራ ብቻ ነው የሚልም ነበረበት።
በመድበሉ ውስጥ ከተካተቱት ታሪኮች ውስጥ አንተ በግልህ የወደድከውና በቀዳሚነት የምታስቀምጠው የትኛውን  ነው?  ደራሲውን ሳትጠቅስ ርዕሱን ብቻ ልትነግረኝ ትችላለህ----?
በዳኝነቱ ውስጥ ባልሳተፍም እኔም ስራዎቹን የማንበብ እድሉ ነበረኝ። አጋጣሚ ሆኖ ወደ ጀርመንኛ እንዲተረጎሙ በዳኞች የተመረጡት ሦስት ስራዎች እኔም ይበልጥ የወደድኳቸው ናቸው። “የክራሩ ክር”፣ “ኩኩ ሉሉ” እና “የማልረሳው መረሳት”።  
ከዲጂታል ሚዲያ መስፋፋት ጋር ተያይዞ አጭር ልብወለድን ጨምሮ ጠብሰቅ ያሉ የፈጠራ ሥራዎች ተዳክመዋል የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ አንተ በዚህ ሃሳብ ትስማማለህ?
ሁልጊዜም ዘመን የራሱ መልክ አለው። የዲጂታል ሚዲያ መስፋፋት ከኛ ቁጥጥር ውጪ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ተጽዕኖው ሁለንተናዊ መሆኑን ልንክደው አይቻለንም። ስለዚህ መፍትሄ የሚሆነው መገዳደር ሳይሆን፣  ይህንን ዘመን አመጣሽ ቴክኖሎጂ እንዴት አድርጌ ነው እኔ ለምሰራው ጉዳይ የምጠቀምበት፣ ምን አይነት ኦዲየንስ ነው ያለው፣ ወዘተ የሚለው ነው መታሰብ የሚኖርበት። በአሁኑ ጊዜ በዓለም ላይ የሚወጡ የስነ ጽሑፍ ስራዎች በህትመትም በዲጅታልም እንዲሆኑ እየተደረገ ነው። በሀገር ውስጥም በውጭ ሀገርም ሰራዎቻቸውን በማህበራዊ ሚዲያ ላይ ሲያወጡ ቆይተው፣ ምርጥ ምርጥ ስራዎችን ወደ ህትመቱ ገበያ ያመጡ ብዙ ጸሐፍት አሉ።  ስለዚህ በእኔ በኩል መዳከም ሳይሆን ዲጂታል ሚዲያው በሚፈልገው መልኩ የስነ ጽሑፍ ስራ ቅርፁንም ሆነ አቀራረቡን እየቀየረ ነው በሚል መውሰድ ይሻላል ባይ ነኝ።     
በዚህ መድበል ዝግጅት ውስጥ የጀርመን ባህል ተቋም ሚና ምንድን ነው?
ከጽንሰቱ ጀምሮ እስከ ውልደቱ የባህል ተቋሙ ኃላፊነት ነበር። በሃሳብም ሆነ በገንዘብ።


ሮክስቶን በ1ቢ.ብር የመኖርያ አፓርትመንቶች እየገነባ ነው


         የጀርመኑ ሪልእስቴት ሮክስቶን ኢትዮጵያ፤ ታዋቂዋን ተዋናይት፣ የሚዲያ ባለሞያና ግንባር ቀደም የአረንጓዴ ልማት ተሟጋች አርቲስት አምለሰት ሙጬን፣ የከፍታ አፓርትመንቶች ብራንድ አምባሳደር አድርጎ መሾሙን ሰሞኑን  አስታውቋል፡፡
የዛሬ አራት ዓመት ገደማ ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት በሪልእስቴት ኢንቨስትመንት ላይ የተሰማራው ሮክስቶን ኢትዮጵያ፤ በመዲናዋ  ሲግናል አካባቢ በ1 ቢሊዮን ብር  በጀት ከፍታ በአዲስ አበባ የተሰኘ የመኖሪያ አፓርትመንቶች እያስገነባ ሲሆን አፓርትመንቶቹ ከ30 ሚሊዮን ብር እስከ 150 ሚሊዮን ብር ያወጣሉ  ተብሏል፡፡
አርቲስት አምለሰት ሙጬ የከፍታ አፓርትመንቶች አምባሳደር ሆና መመረጧን አስመልክቶ ባለፈው ረቡዕ በሃያት ሬጀንሲ ሆቴል የሮክስቶን ኢትዮጵያ ከፍተኛ አመራሮችና አርቲስቷ በተገኙበት ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡ ሲሆን፤ የስምምነት ፊርማም ተፈራርመዋል፡፡  
 አርቲስት አምለሰት ሙጬ በብራንድ አምባሳደርነት የተመረጠችበት ዋነኛው ምክንያት አረንጓዴ ዓለምን ለመፍጠር በሚደረጉ ሁለንተናዊ ተሳትፎዎች ላይ እውቅናዋን ተጠቅማ የተለያዩ ንቅናቄዎችን ማሳካት በመቻሏ ነው ያለው ሮክስቶን ሪልእስቴት፤ ከዚህ በተጨማሪም አርቲስቷ ያላት ሰብዕና፣ ቁርጠኝነትና ትልልቅ ራዕዮቿ በሙሉ ድምፅ እንድትመረጥ አድርገዋታል ብሏል።
 አርቲስት አምለሰት አምባሳደርነቷን አስመልክቶ በሰጠችው ማብራሪያ፤ “ዘላቂነት ካለው የሪልእስቴት ልማት ኩባንያ ጋር አብሬ በመስራቴ በጣም ደስተኛ ነኝ። ከፍታ፤ አዲስ አበባን የሚያምር ገፅታ በማላበስ፣ አረንጓዴነቷን በማስቀጠል የተፈጥሮ ሀብትን ለትውልድ እያስቀጠለ የሚገኝ ፕሮጀክት ነው። በተጨማሪም እኔ እራሴ በከፍታ አፓርትመንት የቤት ባለቤት በመሆኔ  ኩራት ይሰማኛል፡፡” ብላለች፡፡
 ለብራንድ አምባሳደርነቷ ምን ያህል እንደተከፈላት ከጋዜጠኞች የተጠየቀችው አምለሰት፣ የክፍያውን መጠን ለመናገር ፈቃደኛ ሳትሆን የቀረች ሲሆን ይልቁንም፤ ”አንድ ቤት የሚሰጡኝ ይመስለኛል፤ፔንትሃውስ ቢሆን ደስ ይለኛል፡፡” ስትል በቀልድ ተናግራለች፡፡
ከኩባንያው ጋር ለመሥራት የተስማማሁት ለአካባቢ ጥበቃ ትኩረት የሚሰጥ በመሆኑና በህንጻዎቹ ዲዛይን ላይ የኢትዮጵያን ባህልና ታሪክ በማንጸባረቁ ነው ብላለች - አርቲስት አምለሰት፡፡
የሮክስቶን መሥራችና ዋና ሥራ አስፈፃሚው ሚስተር ዲትሪክ ኢ. ሮጄ ስለ አምለሰት በብራንድ አምባሳደርነት መመረጥ ሲናገሩ፤ “አርቲስት አምለስት ባላት የግል ማንነት ከፍታ የያዘውን የዘመናዊነትና የአካባቢ ጥበቃ ተነሳሽነት ለብዙ ደንበኞቻችን ለማሳየት ወሳኝና ተመራጭ እንስት ናት። በአስገራሚ ሰብዕናዋና ከማህበረሰቡ ጋር ባላት ጠንካራ ትስስር፣ ተፅዕኖ የመፍጠር አቅሟ ከፍተኛ ስለሆነ ከፍታ አፓርትመንቶችን በማስተዋወቅ እንዲሁም አዲስ ነገሮችን በጋራ የመፍጠር ራዕያችንን ታሳካለች ብለን እናምናለን፡፡” ብለዋል፡፡
 የሮክስቶን ኢትዮጵያ  ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ አድያምሰገድ ኢያሱ በበኩላቸው፤ “አርቲስት አምለሰት ሙጬ ብራንድ አምባሳደራችን በመሆኗ በጣም ደስተኞች ነን። አምለሰት የእኛን የልህቀት፣ የጥራትና የማህበራዊ ሀላፊነት እሴቶች የምትጋራ መልካም ሰብዕና ያላት ድንቅ አርቲስት ናት። ለድርጅታችን ትልቅ ሀብት እንደምትሆንና ወደምንፈልጋቸው ደንበኞቻችን እንዲሁም ባለድርሻ አካላት እንድንደርስ ትረዳናለች ብለን እናምናለን” ሲሉ ተናግረዋል፡፡
  ሮክስቶን ሪልእስቴት በጀርመን የተመሰረተ በግንባታው ዘርፍ ሙሉ አገልግሎት የሚሰጥ የሪልእስቴት ገንቢና የኢንቨስትመንት ድርጅት ሲሆን፤ በጀርመን ስፔንና ፖርቹጋል በየተለያዩ ፕሮጀክቶችን ማከናወኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡   


ESX ወደ ሥራ ለመግባት ተጨማሪ 625 ሚ ብር ያስፈልገዋል
                      

       ዘመን ባንክ 47.5 ሚሊዮን ብር በኢትዮጵያን ሴክዊሪቲ ኤክስቼንጅ ላይ ኢንቨስት ማድረጉን ያስታወቀ ሲሆን፤ የኢትዮጵያን ሴክዊሪት ኤክስቼንጅ (ኢኤስኤክስ) በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ ስራ ለመግባት 625 ሚሊዮን ብር ተጨማሪ ኢንቨስትመንት ያስፈልገዋል ተብሏል።
በሳምንቱ አጋማሽ ላይ በዘመን ባንክ ዋና መሥርያ ቤት  በተፈረመው የኢንቨስትመንት ውል  መሰረት ዘመን ባንክ በኢትዮጵያን ሴክዊሪቲ ኤክስቼንጅ 5% ድርሻ መያዙ ተረጋግጧል። የዘመን ባንክ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ደረጀ ዘበነ እንደተናገሩት፤ ኢኤስኤክስ ገዢና ሻጭን፤ ፈላጊና ተፈላጊን የማገናኘት ሥራ የሚያከናውን ሲሆን፤ የካፒታል ገበያው እንዲያድግና የአገር ኢኮኖሚ እንዲቀየር በማገዝ ትልቅ ሚና እንደሚጫወት ተነግሯል፡፡ የዘመን ባንክ ዳይሬክተሮች ቦርድ በኢኤስኤክስ ላይ ኢንቨስት ለማድረግ ሲወስን የባንኮችን የኢንቨስትመንት ገደብ ባማከለ መንገድ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ዘበነ፤ በሌሎች የዓለም ክፍሎች ያለውን የገበያ ስርዓት በኢትዮጵያ እውን ማድረግ እንደሚያስፈልግም አሳስበዋል። ባንኮችና የፋይናንስ ተቋማት በአርአያነት እንደሚከተሉን አምናለሁ ያሉት የባንኩ ሥራ አስፈፃሚ፤ የሴክዊሪቲ  ኤክስቼንጅስ መዋቅር መዘርጋቱ ተቋማት ወደ ገበያ እንዲወጡና ሃብት መፍጠር እንዲችሉ መንገድ  እንደሚያመለክታቸው ተናግረዋል፡፡
”ዘመን ባንክ ከESX ጋር ተባብሮ ለመሥራት ኢንቨስት በማድረግ ከመጀመሪያዎቹ  አንዱ በመሆኑ በጣም ደስተኞች ነን፤ የካፒታል ገበያ መስፋፋት በኢትዮጵያ የፋይናንስ ዘርፎች ላይ ለውጥ ያመጣል፣ ስለዚህም በዚህ አስደሳች ጉዞ ውስጥ በመቀላቀላችን ተደስተናል።” ብለዋል፤ ዋና ሥራ አስፈጻሚው፡፡
የኢትዮጵያን ሴኪዩሪቲስ ኤክስቼንጅ (ኢኤስኤክስ) ሙሉ በሙሉ ወደ ስራ ሲገባ ኩባንያዎች፤ ባንኮችና ኢንሹራንሶች ሲቋቋሙም ሆነ ሲስፋፉ አክሲዮኖቻቸውን ይሸጥላቸዋል። ዋናው አገልግሎቱም አዲስ ለሚመሠረቱም ሆነ ለነባር ኩባንያዎች የካፒታል ገበያን መፍጠር ነው ተብሏል፡፡
የESX ዋና ሥራ  አስፈፃሚ ዶክተር ጥላሁን እሸቱ ካሳሁን በበኩላቸው፤ መ/ቤታቸው የካፒታል ገበያን ለማስተዋወቅ ባለፉት ሁለት ዓመታት ሲሰራ መቆየቱን ይገልፃሉ። ፈጣን የንግድ መፍትሄዎችን በማዘጋጀት ፣ አዳዲስ ሠራተኞችን በመቅጠርና የተለያዩ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን በሚያከናውኑበት ወቅት  የዘመን ባንክ ኢንቨስትመንት መምጣቱን አመሥግነዋል። የኢትዮጵያን ሴኪዮሪትስ ኤክስቼንጅ በ900 ሚሊየን ብር ካፒታል ለመገንባት መታቀዱን የተናገሩት ዋና ስራ አስፈፃሚው ዶክተር ጥላሁን እሸቱ፤ ባለፈው ሁለት ዓመት ውስጥ ሃምሣ በመቶ ጊዚያቸውን የወሰደው ስለ ካፒታል ገበያው የማሳመን፤ የማስረዳትና የማስተዋወቅ ስራ እንደነበር አስረድተዋል፡፡
መንግስትና ሌሎች አጋር ተቋማት እስከ  25 % ድርሻን በመግዛታቸው 225 ሚሊዮን ብር መገኘቱን የገለፁት ስራ አስፈፃሚው፤ የተቀረውን 625 ሚሊዮን ብር ካፒታል ለመሙላት ከአገር ውስጥ የፋይናንስ ተቋማትና ኩባንያዎች እንዲሁም በውጭ ምንዛሬ ከባህርማዶ የፋይናንስ ተቋማት ለመሰ ብሰብ እንቅስቃሴ እያደረግን ነው ብለዋል። አጠቃላይ ሂደቱም መንግስትና የግሉ ዘርፍ አንድ ላይ መሥራት እንደሚችሉ ማሣያ እንደሚሆንም ዶ/ር ጥላሁን ጠቁመዋል፡፡”ከ10 ሚሊየን እስከ 150 ሚሊየን ብር ኢንቨስት በማድረግ የኢትዮጵያን ሴኪዩሪቲ ኤክስቼንጅስ ድርሻን መግዛት ይቻላል። በኢትዮጵያ የሚንቀሳቀሱ 30 ባንኮችና 18 የኢንሹራንስ ኩባንያዎች አብረውን እንዲሰሩ  እንፈልጋለን“ ብለዋል፤የESX ዋና ሥራ  አስፈፃሚው፡፡