Administrator

Administrator

   • ለፍቅሩ ሲል ብቻ ኢትዮጵያን በመላው ዓለም ያስተዋውቃል
                       • ለቱሪስቶች ብቁ፤ ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቀ አገልግሎት መስጠት አለብን
                       • ‹‹The Grate Run Of Ethiopia›› በቱሪዝም ማስታወቂያ ላይ የተሰራ ግድፈት?!
                       • የሬጌ ሙዚቃ ለኢትዮጵያ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ዋና የፕሮሞሽን መሳርያ ነው
                      • ሆቴሎች የሚያሰማሯቸው ሰራተኞች በከፍተኛ ደረጃ የሰለጠኑ ሊሆኑ ይገባል

      ራስ ሊቫይ ይባላል፡፡ በመዝገብ ስሙ  ማርክ ጆን ባፕቲስት ቬነስ ተብሎ የሚጠራ ሲሆን ፤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ኃይማኖት የተጠመቀበት የክርስትና ስሙ ደግሞ አምደስላሴ ነው፡፡ በካረቢያን በምትገኝና ማርቲኔክ በተባለች ደሴት የተወለደው ራስ ሊቫይ፤ ከወጣትነቱ ጀምሮ የስደት ህይወቱን ያሳለፈው በአውሮፓ  ነበር፡፡ በፈረንሳይና በእንግሊዝ   በሚገኙ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ተምሯል፡፡ በቢዝነስና ማርኬቲንግ ፣ በኢንተርናሽናል ቱሪዝምና ሆቴል አስተዳደር እንዲሁም በእንግሊዝኛና ፈረንሳይኛ ቋንቋዎች ተርጓሚነት ከፍተኛ ትምህርቶችን በመከታተል ተመርቋል፡፡
በእንግሊዟ የለንደን ከተማ ያለፉትን 30 ዓመታት የኖረው ራስ ሊቫይ፤ ወደ ኢትዮጵያም  ሲመላለስ  ከ20 ዓመታት በላይ አስቆጥሯል፡፡  በፓን አፍሪካኒዝምና በራስ ተፈርያኒዝም ዓለም አቀፍ እንቅስቃሴዎች ንቁ ተሳትፎ እንደሚያደርግ ይናገራል፡፡ የኢትዮጵያ፤ የአፍሪካ፤ የካረቢያን አገራትና በመላው ዓለም ያሉ ጥቁር ህዝቦች ታሪክን በጥልቀት ሲያጠና የኖረው ራስ ሊቫይ፤ በኢትዮጵያ ላይ ያተኮሩ የተለያዩ ጽሁፎችን ዓለም አቀፍ ተነባቢነት ባላቸው መፅሄቶች፣ ጋዜጦችና የተለያዩ የሕትመት ውጤቶች ላይ ያወጣል፡፡ በዓለም አቀፍ የቱሪዝምና የሆቴል አስተዳደር ባለሙያነቱ ደግሞ ለኢትዮጵያ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ እገዛና ድጋፍ እንደሚያደርግ ይገልጻል፡፡ በክልሎችና የከተማ መስተዳድሮች ከሚንቀሳቀሱ የቱሪዝም ቢሮዎች ጋር የበጎ ፍቃድ አማካሪ ሆኖ በማገልገል ዕውቅናና ምስጋና ተቀዳጅቷል፡፡  ዋንኛ መተዳደሪያው የንግድ ስራ ሲሆን የኢትዮጵያን ባሕላዊ አልባሳት፤ ጌጣጌጦችና ሌሎች ቁሳቁሶች ወደ ለንደን በመውሰድ ይሸጣል፡፡ በተጨማሪም የመፅሐፍትና የተለያዩ የህትመት ውጤቶች አከፋፋይም እንደሆነ ይናገራል፡፡ የእሱ ህልም ግን በሚወዳት ኢትዮጵያ የሥራ ፈቃድ አግኝቶ፣ለአገሪቱ በአቅሙ አስተዋጽኦ ማበርከት ነው፡፡ ይሄ ሁሉ ፍቅርና መቆርቆር ከየት የመጣ? ከፍቅር በፊት ዕውቀት ይቀድማልና ኢትዮጵያን እንዴት በጥልቀት ሊያውቃት ቻለ? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ግሩም ሰይፉ ከራስ ሊቫይ ጋር ባደረገው ጥልቅ ቃለ-ምልልስ ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ አግኝቷል፡፡ በኢትዮጵያ ቱሪዝም ዙሪያም በስፋት አውግተዋል፡፡ የኢትዮጵያ የቱሪዝም ኢንዱስትሪን ለማዘመንና ስኬታማ ለማድረግ የሚበጁ ዕውቀቶችንና አቅጣጫዎችን ከቃለምልልሱ ማግኘት ይቻላል፡፡ እነሆ ፡-

           እስቲ መጀመሪያ ስለ ትውልድ አገርህ ማርቲኔክ ትንሽ አስተዋውቀን…?
ማርቲኔክ በካረቢያን ባህር ምስራቃዊ ክፍል የምትገኝ ደሴት ናት፡፡ በ16ኛው መቶ ክፍለ ዘመን  የፈረንሳይ ቅኝ ግዛት ነበረች፡፡ በተለያዩ ጊዜያት ስፔንና እንግሊዝም በቅኝ ገዢነት  ተፈራርቀውባታል። ፈረንሳይኛ ዋናው የስራ ቋንቋ ቢሆንም  እንግሊዘኛና ስፓኒሽ ቋንቋዎች በስፋት የሚነገሩባት አገር ናት። ማርቲኔክ፤ ከመላው አውሮፓ፣ ከአሜሪካ፣ ከደቡብ አሜሪካ የሚመጡ  ቱሪስቶች ይጎበኟታል፡፡ በካረቢያን ሌሎች አገራትና ደሴቶች የሚገኙ ህዝቦችም እንደ ሁለተኛ አገራቸው ይመለከቷታል፡፡ በተለይ ከትሪንዳድ፤ በርባዶስ፤ ጃማይካ፤ ሴንት ሉሽያ፤ ከጓደሉፕ፤ ግሬኔዳ እና ሴንት ማርቲን የሚፈልሱ ህዝቦች መጠጊያ የሆነች ውብ ምድር ነች፡፡
ማርቲኔክን የአበባዎች ደሴት  ብሎ መጥራትም ይቻላል፡፡ በተለይ ሞቃታማ የአየር ንብረት የሚስማማቸው የአበባ ዝርያዎች በደሴቷ ላይ በብዛት ስለሚበቅሉ ልዩ የተፈጥሮ ውበት አጎናፅፈዋታል። የማርቲኔክ ህዝብ በየደጁ አበባ በማብቀል ባህሉም ይታወቃል፡፡ በመላው ማርቲኔክ ስትዘዋወር በየቦታው፣ በየመንገዱ፣ በየአደባባዩ፣ በየመናፈሻውና በየመኖርያ ቤቶች ግቢ በተለያየ ቀለማት የደመቁ የአበባ ተክሎችን ስትመለከት በአድናቆት ነው የምትፈዘው፡፡  በአትክልትና ፍራፍሬ አምራችነትና አከፋፋይነት የምትታወቅም ሲሆን በተለይ ለዓለም ገበያ ከምታቀርብባቸው የፍራፍሬ አይነቶች ሙዝና አናናስ ይጠቀሳሉ፡፡ በሌላ በኩል የተጣራ ነዳጅ ለዓለም ገበያ የምታቀርብ ሲሆን ‹‹ራም›› የተባለ ባህላዊ የአልኮል መጠጥ አምራችም ነች፡፡
አገርህን አሳምረህ ስላስተዋወቅከን አመሰግናለሁ። አሁን ወደ ኢትዮጵያ እንምጣ፡፡ እስቲ በኢትዮጵያ ላይ ስለምታቀርባቸው የፅሁፍ ስራዎች ልጠይቅህ---
 ኢትዮጵያን የሚመለከቱ ፅሁፎችን በለንደን ከተማና በድረገፅ በዓለም ዙርያ በሚሰራጩ የተለያዩ ሚዲያዎች ላይ አቅርቤአለሁ፡፡ በ2004 እ.ኤ.አ የቦሌ ዓለም አቀፍ ተርሚናል መገንባቱን አስመልክቶ ያዘጋጀሁት ፅሁፍ የመጀመርያው ነበር፡፡ በእንግሊዝና በካረቢያን አገራት  ከፍተኛ ተነባቢነት ባለው የጃማይካ ጋዜጣ ‹‹ዘ ግሊነር›› ላይ ለህትመት በቅቷል፡፡ ከዚያም ‹‹ኢስት አፍሪካን›› በተባለና በእንግሊዝ በሚታተም መፅሄት ላይ በተከታታይ ፅሁፎችን ማቅረብ ቀጠልኩ፡፡ በ2007 እ.ኤ.አ ላይ ኢትዮጵያ የሚሊኒዬም በዓሏን ስታከብር በዓለም አቀፍ ደረጃ በሚታወቀው ‹‹ራስታአይትስ›› ድረ-ገፅ ልዩ መጣጥፍም አቅርቤያለሁ፡፡ በተመሳሳይ ወቅት ለንደን ውስጥ በአማርኛና በእንግሊዘኛ ቋንቋዎች በታተመና የኢትዮጵያ ማህበረሰብ ባዘጋጀው መፅሄት ላይ ሚሊኒዬሙን ምክንያት በማድረግ በ3 የተለያዩ አጀንዳዎች ፅሁፎችን በማዘጋጀት አስነብቤም ነበር፡፡ ከየአፍሪካ ህብረት 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓል ጋር በተገናኘ ያዘጋጀሁት ጽሁፍም ተጠቃሽ ነው፡፡
ለኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፍ ስላደረግሃቸው እገዛዎችና ድጋፎች በዝርዝር ልትነግረኝ ትችላለህ?…
በለንደን በሚገኝ ዩንቨርሲቲ ኢንተርናሽናል ቱሪዝምና ሆቴል አስተዳደር በምማርበት ወቅት በኢትዮጵያ ቱሪዝም ላይ የጥናት ፅሁፍ የምሰራበት እድል መፈጠሩ ዋንኛው መነሻ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ላለፉት 20 ዓመታት በኢትዮጵያ የቱሪዝም እንቅስቃሴዎች የተለያዩ አስተዋፅኦዎች ለማበርከት ሞክሬአለሁ፡፡ የቱሪዝም ዘርፍ ላይ ልዩ ትኩረት ማድረግ የጀመርኩት በ2007  የኢትዮጵያ ሚሊኒዬም ክብረ በዓል ጋር በተያያዘ ነበር።  በ2009፤ በ2012 እና በ2013 በተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎች በመዘዋወር ካደረግኋቸው ጉብኝቶች ጎን ለጎን ያከናወንኳቸው ተግባራትም ነበሩ፡፡ በ2009 በደቡብ ክልል የተለያዩ ከተሞችን ጎብኝቼአለሁ፡፡ በክልሉ የሚገኙ የተፈጥሮ ሃብቶች፣ ባህላዊ እሴቶች፣ አኗኗርና አመጋገብን የተመለከተ ልዩ ፅሁፍ ያዘጋጀሁበት ጉብኝት ነበር። ከተሞቹ ከደቡብ ካረቢያን አገራት ጋር በብዙ ሁኔታዎች መመሳሰላቸውን ያሳየሁበት ይህ ፅሁፍ፤ የደቡብ ክልልን የቱሪዝም መዳረሻዎች በማስተዋወቅ ረገድ ስኬታማ ነበር፡፡ ከክልሉ የቱሪዝም ቢሮም የምስጋና ወረቀት አግኝቼበታለሁ፡፡
ከሃዋሳ ከተማ የቱሪዝም ቢሮ ጋር በፈጠርኩት ግንኙነት በተለያዩ የቱሪዝም ማስተዋወቂያ ህትመቶች ዝግጅት ላይ የአርትኦት፣የትርጉምና የማማከር ስራዎችን በማከናወን ተሳትፌያለሁ፡፡ ከዚያም በአዲስ አበባ ለባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ተመሳሳይ እገዛዎችን አድርጌያለሁ፡፡ በትግራይ ከመቀሌ ከተማ የቱሪዝም ቢሮ ጋር የክልሉን የቱሪዝም መስህቦች ለማስተዋወቅ በዲቪዲ በተዘጋጀ ፊልም ላይ በትርጉምና በአርትኦት ስራዎች ተሳትፌአለሁ፡፡ በአንድ ወቅት በአርባ ምንጭ በተካሄደ የቱሪዝም ሴሚናር ላይ ያለኝን እውቀትና ልምድ ያካፈልኩበት አጋጣሚም ነበር፡፡ በ2013 በታላቁ የህዳሴ ግድብና በኢትዮጵያ የመሰረተ ልማትና የኢኮኖሚ እድገቶች ላይ የሚያተኩር ብሮሸር አዘጋጅቼ በመላው አውሮፓ፤ በአሜሪካና በሰሜን አሜሪካ በማሰራጨትም ተሳክቶልኛል። ይህን ብሮሸር ሙሉ ወጭውን በመሸፈን  ነው ያዘጋጀሁት፡፡ አሁን 3ኛው ህትመት የሚያስፈልግበት ደረጃ ላይ ነው፡፡ በተመሳሳይ ወቅት በእንግሊዝ በሚገኙ የራስ ተፈርያን ማህበረሰብ በሚዘጋጅ ‹‹ተንደር›› በተባለ  መፅሄት ላይ ስለ ኢትዮጵያ ቱሪዝም የተለያዩ መረጃዎች ያሉበት፤ ለቱሪስቶች ምክር የሚሰጥ  ፅሁፍም አሳትሜ ነበር፡፡
ለኢትዮጵያ ቱሪዝምን ያስተዋውቃል ተብሎ ስለተሰራው ስህተት የበዛበት ቡክሌት እናውራ።  ግን መጀመሪያ ስለ ቡክሌቱ ለአንባቢዎች ጥቂት ነገር መግለፅ የሚያስፈልግ ይመስለኛል፡፡ በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከ2 ዓመት በፊት የተዘጋጀው ቡክሌቱ 34 ገፆች ያሉት ሲሆን በመላው ዓለም ተሰራጭቷል፡፡ የፊትና የጀርባ ሽፋኖቹን በተራሮች ያስጌጠ ነው፡፡ በመጀመርያው ገፅ ላይ ‹‹የቱሪዝም ገነት›› በሚል ርእስ መረጃዎች አስቀምጧል። በሌሎች ገፆች ደግሞ በኢትዮጵያ ከፍተኛ ጎብኚ ያላቸው የቱሪዝም መዳረሻዎች በተከታታይ ከፎቶና ከአጫጭር መግለጫዎች ጋር ታትሞበታል፡፡ የጎንደር ፋሲለደስ ቤተ መንግስት፤ በላሊበላ የሚገኘው የቅዱስ ጊዮርጊስ ውቅር ቤተ ክርስትያን፤ የአክሱም ሐውልት፣ በአፋር ክልል የሚገኘው የእሳተ-ጎመራ ልዩ የተፈጥሮ መስህብ - ኤርታሌ፤ የሀረር ግንብ፤ የሰሜን ተራራዎች ፓርክና ጥያ የድንጋይ ትክል በአጫጭር መግለጫዎች ከታጀቡ ፎቶዎች ጋር ቀርበዋል፡፡ ከዚያም ዝቅተኛዎቹ የአዋሽና ኦሞ ሸለቆዎች፤ የኮንሶ መልክዓምድር፤ ልዩ ልዩ ፌስቲቫሎች፡- (አሸንዳ፣ መስቀል፣ ኢሬቻ፣ ገና እና ጥምቀት፤….) በቡክሌቱ እንዲተዋወቁ ተደርጓል፡፡
በጣም የሚገርምው ይህን ቡክሌት የተቀበልከው ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣትህ በፊት በለንደን ከተማ የተለያዩ አገራት የቱሪዝም ኢንዱስትሪያቸውን በሚያስተዋውቁበት ዝግጅት ላይ ሲሰራጭ ነው። ወደ ኢትዮጵያ ስትመጣ በቡክሌቱ ይዘት ላይ ብዙ ስህተቶች መኖራቸውን ካሳየኸኝ በኋላ ነው ይህን ቃለ-ምልልስ ለመስራት የወሰንኩት፡፡ እስቲ በቡክሌቱ ላይ የታዘብከውን ስህተቶች አጫውተኝ ------
ስለ ኢትዮጵያ ብዙ የማውቅና በየጊዜው ተመላልሼ የምመጣ ቢሆንም፤ እንደ ማንኛውም የውጭ አገር ዜጋ መረጃዎች እፈልጋለሁ፡፡ ስለዚህም የጠቀስከውን የቱሪዝም ቡክሌት ለንደን ከተማ ላይ እያገላበጥኩ የተመለከትኩት በቁጭት ነበር፡፡ የቡክሌቱን ይዘት አብረን እንደተመለከትነው፣በየገፁ በተፃፉት የእንግሊዘኛ ቃላት በርካታ የስፔሊንግ ስህተቶች አሉባቸው። የእንግሊዘኛ ሰዋሰውን ብንፈትሸውማ -- ተወው፡፡ በየገፁ የተቀመጡት ፈዛዛ ፎቶዎችና ማራኪ ያልሆኑ የምስል ዲዛይኖችም ህትመቱ በቂ ትኩረት ተሰጥቶት አለመሰራቱን ያመለክታሉ፡፡  ምንም አይነት ፅሁፍም ሆነ ፎቶ ሳይኖረው ባዶውን የተተወ ገፅ መገኘቱም የሚያስደነግጥ ነው፡፡
ሌላው አስደንጋጭ ስህተት ደግሞ የመጨረሻው የሽፋኑ የውስጥ ገፅ ላይ የተመለከትከው ነው፡፡ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ዓመታዊ የ10 ኪሜ የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር ምስሎች በቀረቡበት በዚህ የሽፋን ገፅ፤ በትልቁ ጎልቶ የሰፈረው ፅሁፍ ‹‹The Grate Run Of Ethiopia›› ይላል፡፡ ‹‹The Great Ethiopian Run›› ለማለት ነው። ለቱሪዝም ኢንዱስትሪው  የላቀ አስተዋፅኦ እያበረከተ ስለሚገኘው  ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ላይ እንዲህ የጎላ ግድፈት መፈጠር አልነበረበትም፡፡ ስለ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ እኮ በእንግሊዝ ብዙዎች ያውቃሉ፡፡ በተሳሳተ መንገድ ማስተዋወቁ ልክ አይደለም፡፡ በየዓመቱ ከ750 በላይ የውጭ አገር ዜጎች የሚያሳትፈው የጎዳና ላይ ሩጫው፤ በስህተት መተዋወቁ ለትዝብት እንደሚዳርግ መታሰብ ነበረበት፡፡ በርግጥ በጥራት የተሰሩ ሌሎች ቡክሌቶች፤ የተለያዩ ፓምፍሌቶችና በራሪ ወረቀቶች በመላው ዓለም መሰራጨታቸውን አውቃለሁ፡፡ ግን በዚህ ቡክሌት ላይ ያሉት ስህተቶች የኢትዮጵያን ቱሪዝም  በማስተዋወቅ ረገድ ብዙ መስተካከል ያለባቸው ሁኔታዎች እንዳሉ ያስገነዝቡናል፡፡
ወደ አዲስ አበባ ከወር በፊት እንደመጣሁ ብዙ የግል ስራዎች ቢኖሩብኝም፤ ለኢትዮጵያ ሁሌም ቅድሚያ ስለምሰጥ በቡክሌቱ ላይ ያሉ ግድፈቶችን በተመለከተ ከማውቃቸው የቱሪዝም ሰዎች ጋር ለመነጋገር ሞክሬአለሁ፡፡ ከሳምንት በፊት ከአንተ ጋር ተገናኝተን የቡክሌቱን ግድፈቶች ስንታዘብ ቆይተን በበጎ ፈቃደኝነት ‹‹ይህን ቡክሌት ሙሉ ለሙሉ የአርትኦት ስራውን ልስራው፤ ቢያንስ በአማካሪነት ላግዛችሁ›› በሚል በቀጥታ ከቱሪዝም ሃላፊዎች ጋር በድረገፅ በኩል ባገኘሁት የኢሜል አድራሻዎች ግንኙነት ለመፍጠር ሞክሬ ነበር፡፡
በአጠቃላይ እኔ ይህን ስህተት በግልፅ የምተቸው የአገሪቱን ገፅታ ለማሳጣት፤ አርትኦት በመስራት ልጠቀም ብዬ አይደለም፡፡ ሁልጊዜም ማየት  የምፈልገው የኢትዮጵያን መልካም ገፅታ ነው፡፡ እናም ቁጭቴ፣ አገሪቱ ደረጃውን በጠበቀና በአግባቡ በሚሰሩ ህትመቶች ለሌላው ዓለም መተዋወቅ ይኖርባታል የሚል ነው። እንግሊዘኛ ዓለም አቀፍ  ቋንቋ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ስለዚህም በዚህ ቋንቋ ተፅፈው ለቱሪዝም ማስተዋወቂያ ይሆናሉ በሚል የሚሰሩ ማናቸውም ህትመቶች ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የሚያሟሉ፤ ምንም አይነት ስህተት የሌለባቸው፤ በትኩረት የተዘጋጁ መሆን አለባቸው፡፡ በሌላ በኩል የኢትዮጵያን ቱሪዝም በእንግሊዝኛ ብቻ ሳይሆን በሌሎች ቋንቋዎችም ለማስተዋወቅ ጥረት ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ የቱሪዝም መስኩ ከአማርኛና እንግሊዘኛ ባሻገር ተጨማሪ ሌሎች ቋንቋዎች ያስፈልጉታል፡፡ በተለይ ፈረንሳይኛ ወሳኝ ሲሆን በአፍሪካ ብዙ አገራት ፈረንሳይኛ ቋንቋ እንደሚናገሩ ይታወቃል፡፡ ስለሆነም ለማስተዋወቅ የሚዘጋጁ ህትመቶች ፈረንሳይኛ ቢጨመርባቸው ጠቃሚ ነው፡፡ ከተቻለ ደግሞ አረብኛና ስፓኒሽ ቋንቋዎች እንዲሁም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ቻይናውያን ቱሪስቶች እንደ መብዛታቸው የእነሱን መንደሪን ቋንቋ የሚያውቁ ባለሙያዎች መፈጠር አለባቸው። ቋንቋዎችን በብዛት ማወቅ ለቱሪስቶች መስጠት የሚቻለውን አገልግሎት ማጠናከር ብቻ ሳይሆን ዓለም አቀፍ መግባባትን መፍጠር ነው፡፡
ከ2 ዓመት በፊት ኢትዮጵያ በአውሮፓ የቱሪዝምና የንግድ ምክር ቤት ‹‹የዓለማችን ምርጥ የቱሪዝም መዳረሻ›› በሚል ተመርጣ ነበር፡፡ ጁሚያ ትራቭል የተባለ ተቋም  ደግሞ በኢትዮጵያ ቱሪዝም ላይ በማተኮር በሰራው የ2017 ሆስፒታሊቲ ሪፖርት መሰረት፤ በ2016 ላይ ኢትዮጵያ ከ800ሺ በላይ ቱሪስቶች በማስተናገድ 5.6 ቢሊዮን ዶላር ወይንም ከ128 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ አግኝታለች ብሏል፡፡ በሌላ በኩል ዓለም አቀፉ የጉዞና ቱሪዝም ምክር ቤት በኢትዮጵያ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ለ979ሺ ሰዎች የስራ እድል መፍጠሩን በሪፖርቱ አመልክቷል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት እስከ 2020  በቱሪዝም መስክ ከፍተኛ እንቅስቃሴ ለማድረግ ‹‹LAND OF ORIGINS›› የሚል መርህ በማንገብ ተነስቷል፡፡ በየዓመቱ የሚመጡ ቱሪስቶችን በሦስት እጥፍ ለማሳደግ  እቅድ ከመያዙም በላይ ከአፍሪካ 5 ዋንኛ የቱሪስት መዳረሻ የሆኑ አገራት ተርታ ለመሰለፍም እየተሰራ ነው። በአፍሪካ ቱሪስት በብዛት የሚጎበኛቸውና ከፍተኛ ገቢ በማስመዝገብ ሞሮኮና ደቡብ አፍሪካ ግንባር ቀደም ናቸው፡፡  በየዓመቱ እያንዳንዳቸው ከ10 ሚሊዮን በላይ ቱሪስቶች ያስተናግዳሉ፡፡ ግብፅ ደግሞ በየዓመቱ ከ9.9 ሚሊዮን በላይ ቱሪስቶችን በማስተናገድ ትከተላለች፡፡ ሶስቱ አገራት ከፍተኛ የቱሪስት ፍሰት ሊኖራቸው የቻሉት በተጠናከሩ መሰረተ-ልማቶቻቸው እንዲሁም ለቱሪስቶች በሚያቀርቧቸው አገልግሎቶች  እንደሆነ ይገለፃል፡፡ ኢትዮጵያ በዓለም የኢኮኖሚክ ፎረም በተሰራ ጥናት  በምቹ የቱሪዝም መዳረሻነት ገና ብዙ ይቀራታል ተብሏል።  በቱሪዝም መሰረተ ልማቶች በተለይ በመንገድና ሆቴሎች ዙርያ የተሻለ ደረጃ ላይ ብትገኝም ለቱሪስቶች በሚሰጡ አገልግሎቶች ብዙ መሻሻሎች ያስፈልጋሉ፡፡ በአስተማማኝ ፀጥታና ደህንነት፣ በጤና እና ንፅህና፣ በተማረና በሰለጠነ የሰው ሃይል፤ በኢንፎርሜሽንና ኮሚኒኬሽን ቴክኖሎጂ አቅርቦት ዝቅተኛ ደረጃ ላይ ናት፡፡ በቱሪዝም ኢንዱስትሪው በተያዘው እቅድ መሰረት ስኬታማ ለመሆን ምን መደረግ አለበት? ቅድሚያ ትኩረት ሊሰጣቸው የሚገባቸው የትኞቹ ናቸው….?
የመጀመርያው ትኩረት መሆን ያለበት በቱሪዝም መስክ ያለውን የሰው ሃይል በዘመናዊ መልክ ማደራጀት ነው፡፡ ለዚህም ስኬት በስልጠናዎች ላይ መስራት ከፍተኛ ለውጥ ያስገኛል፡፡ በተለይ ወጣቱን ትውልድ የሚያሳትፉ የሰው ሃይል ምልመላዎች፤ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች መኖራቸው ተገቢ ነው።  ለቱሪስቶች ብቁ፤ ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቀና በእውቀት ላይ የተመሰረተ አገልገሎት የሚሰጥበት መዋቅርም መዘርጋት ይኖርበታል፡፡ ከኢትዮጵያ ውጭ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች የሚሰራጩ የቱሪዝም ማስተዋወቂያዎች በአቀራረብ፤ በመረጃቸው ትክክለኛነት፤ በዲዛይን ውበት ደረጃቸውን ጠብቀው መዘጋጀት አለባቸው፡፡ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው የቱሪዝም እንቅስቃሴ ያስፈልጋል። የቱሪዝም እድገት በፈጣን ሁኔታ እንዲቀጥል የሰው ሃይሉ በከፍተኛ ስልጠና እና አደረጃጀት መሻሻል እንዲሁም የማስተዋወቅ ስራዎች ጥራት ወሳኝ መሆናቸው መታወቅ አለበት፡፡ የቱሪዝም ኢንዱስትሪው ወጣቱን ትውልድ የሚያሳትፍ፤ የየክልሉን ማህበረሰብ በባለድርሻ አካልነት የሚያስተባብርና የሚጠቅም፣ ዓለም አቀፍ ደረጃውን በጠበቀ እውቀት የተጠናከረ መሆን ይኖርበታል፡፡
ኢትዮጵያ በቱሪዝም መስክ ግዙፍ አቅም እንዳላትና ብዙም እንዳልሰራችበት በተለያዩ ጊዜያት  የሚወጡ የዓለም አቀፍ ተቋማት ሪፖርተሮች የሚያረጋግጡት ነው፡፡ የቱሪዝም ኢንዱስትሪው የኢኮኖሚ እድገቱን ለማቀላጠፍና በድህነት ቅነሳ የተያዙ አቅጣጫዎችን በመደገፍ ረገድ ወሳኝ መሆኑ መታወቅ አለበት። ማንኛውም የቱሪዝም እንቅስቃሴ ዓለም አቀፍ ግንኙነቶችና ትውውቆችን በማዳበር፤ የኢኮኖሚ እድገት በማቀላጠፍና በማነቃቃት፤ ለማህበረሰቡ ዘላቂ የኢኮኖሚና የባህል እድገት እድሎችን በመፍጠር፤ እና የስራ እድሎችን በማብዛት ከፍተኛ አስተዋፅኦ ይኖረዋል፡፡ ኢንቨስትመንትን የሚያጠናክር፤ የውጭ ምንዛሬን የሚያሳድግ፤ መልካም ገፅታን የሚገነባ መሆኑን መገንዘብም ተገቢ ነው፡፡
በሌላ በኩል የቱሪዝም ኢንዱስትሪውን የሚያበለፅጉ አዳዲስ ሃሳቦችና እቅዶች፤ የአሰራር አቅጣጫዎችን ማበረታታት ያስፈልጋል፡፡ ለምሳሌ ያህል በሙዚቃ ኢትዮጵያን በተሻለ ደረጃ ማስተዋወቅ ይቻላል፡፡ በሬጌ ሙዚቃ እና ራስ ተፈርያኖች በሚሰሯቸው ሙዚቃዎች፣  በሚሳተፉባቸው ትልልቅ መድረኮች ኢትዮጵያን፣አፄ ኃይለስላሴን፤ አዲስ አበባን፤ ሻሸመኔን፤ አድዋን… ደጋግመው ይጠቅሳሉ። የኢትዮጵያ የባንዲራ ቀለማት የፋሽኖቻቸው፤ የመድረኮቻቸው ማድመቂያ ናቸው። ይህ ለቱሪዝሙ መስክ  ትልቅ አቅም የሚፈጥር ነው። ሬጌ  ሙዚቃን፤ የራስተፈርያኖች ባህልና ዓለም አቀፍ እንቅስቃሴን በማስተሳሰር ከኢትዮጵያ ቱሪዝም ጎን በበጎ አስተዋፅኦ እንዲቆሙ ማነሳሳት ይቻላል፡፡ በተለይ የሬጌ ሙዚቃ ለኢትዮጵያ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ዋና የፕሮሞሽን መሳርያ ነው ብዬ ነው የማምነው፡፡ ብዙ የሬጌ ሙዚቀኞች በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ስለ ኢትዮጵያ ይሰብካሉ…የተስፋዋ ምድር እያሉ ያሞግሷታል፡፡ ጓዛቸውን ጠቅልልው መጥተው ሊኖሩባት፤ ሊሰሩባት ይፈልጋሉ፡፡ ይህን በቅርበት ስለማውቅ ሁሌም የማስበው ቢያንስ በኢትዮጵያ በየዓመቱ አንድ ዓለም አቀፍ የሬጌ ሙዚቃ ፌስቲቫል ቢኖር ብዬ ነው፡፡
ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ በገነነችበት የአትሌቲክስ ስፖርትም ቱሪዝሙን ማስተዋወቅ እንደሚቻልም መገንዘብ ጥሩ ነው፡፡ አሁን ለምሳሌ በክረምት ወር 16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በእንግሊዝ ለንደን ይካሄዳል፡፡ ይህን ሻምፒዮና ምክንያት በማድረግ ቱሪዝሙን ለማስተዋወቅ፤ በለንደን ከሚገኘው ኤምባሲ፤ ከዲያስፖራው ማህበረሰብና ከአትሌቲክሱ ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት በመስራት ስኬታማ መሆን አያዳግትም። በአጠቃላይ የኢትዮጵያ ቱሪዝምን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር በሚከተሉት ጉዳዮች ላይ ማተኮር ያዋጣል።  የባለሙያዎች ስልጠናዎች፤ የምክክርና የውይይት መድረኮች፤ ዎርክሾፕ፤ ሴሚናርና ሲምፖዚየም በየጊዜው መዘጋጀት አለባቸው፡፡ ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቀና ዘላቂነት ያለው አሰራር  መኖር አለበት፡፡ በሰላምና መልካም አስተዳደር ዙርያ  የግንዛቤ መፍጠርያ መድረኮችና ልዩ ልዩ ዘመቻዎች በማድረግ ቱሪስቶች አገሪቱን ያለ አንዳች የፀጥታና የደህንነት ስጋት መጎብኘት እንደሚችሉ ማነሳሳት ያስፈልጋል፡፡ በአፍሪካ አህጉር የቱሪዝም ንግድ መረብ የሚዘረጋበትን መዋቅር ኢትዮጵያ በፈር ቀዳጅነት በማስተዋወቅ መስራት ትችላለች፡፡ ከሌሎች አገራት ጋር ጠቃሚ ተመክሮዎችን እንዲሁም ልምዶችን በመለዋወጥ መንቀሳቀስም ይቻላል።
የቱሪዝም ኢንዱስትሪውን ከሚፈታተኑ ጉዳዮች መካከል የአገልግሎት ሰጭ ተቋማት ብቃትና የተሟላ ጥራት ነው፡፡ ማንኛውም ቱሪስት ወደሚጎበኘው አገር ከገባ በኋላ በመጀመርያዎቹ 3 ሰዓታት በሚኖረው ቆይታ ላይ ትኩረት ያደረገ መስተንግዶ ወሳኝ መሆኑን ስትነግረኝ ነበር፡፡ እስቲ ስለሱ አብራራልኝ…
ማንኛውም ቱሪስት የሚጎበኘው አገር ሲደርስ መጀመርያ ላይ እግሩ የሚረግጠው አየር ማረፊያውን  ነው፡፡ ስለዚህም የሚኖረው አቀባበል በቱሪስቱ የእንግድነት መንፈስ ላይ ወሳኝ ተዕእኖ ይኖረዋል፡፡ ይህ አሰራር በካረቢያን አገራት በሚገኝ ልምድ ማጠናከር ይቻላል፡፡ በማርቲኔክ የሚደረገውን በምሳሌነት ልጠቅስልህ እችላለሁ፡፡ ቱሪስቶች በአየር ማረፊያዎችና መርከቦች በሚቆሙባቸው ወደቦች ሲደርሱ በመንግስት የቱሪዝም ተቋም የተደራጁ  የሙዚቃና የባህል ቡድኖች በልዩ ድባብ አቀባበል ያደርጉላቸዋል፡፡ ይህ በኢትዮጵያም ትኩረት ተሰጥቶት መለመድ ያለበት አሰራር ነው፡፡ ወጣቶችን ስልጠና ሰጥቶና አደራጅቶ አገርን ገና ከጅምሩ በሚያስተዋውቁበት ባህላዊ አቀባበል ላይ መትጋት  በቱሪስቱ ላይ የመጀመርያውን በጎ ስሜት የሚፈጥርበት ዕድል አለ፡፡ ቱሪስቱ ከአየር ማረፊያ ከወጣ በኋላ ደግሞ ወደ ሚያርፍበት ሆቴል የሚንቀሳቀስበት የትራንስፖርት አገልግሎትም ቀጣዩ ወሳኝ ነገር ነው፡፡ የትራንስፖርት አገልግሎቶች በተመጣጠነ ዋጋ፤ ምቹ በሆኑ ሁኔታዎች መሰጠት አለባቸው፡፡ የመጨረሻው ወሳኝ አቀባበል የሆቴል አገልግሎት ነው፡፡ የሆቴሎች አገልግሎት ከቱሪዝም ኢንዱስትሪው ጋር የላቀ ትስስር ስለሚኖራቸው በዚህ ላይ ትኩረት መስጠቱ አስፈላጊ ነው፡፡
 ሆቴሎች የኮከብ ደረጃቸውን መጠበቃቸው ብቻ ሳይሆን አገልግሎት ሰጭ ሰራተኞቻቸው በከፍተኛ ደረጃ የሰለጠኑና ደረጃውን የጠበቀ መስተንግዶ ለመስጠት የሚችሉ መሆን አለባቸው፡፡ በተለይ ኢትዮጵያ ውስጥ ከሆቴል አስተናጋጆችና ሌሎች ሰራተኞች ጋር በተያያዘ የማስተውለው የቋንቋ ችግር ነው፡፡ በሆቴል ለቱሪስቶች መስተንግዶ የሚሰጡ ባለሙያዎች ቢያንስ እንግሊዘኛ በተጨማሪም ፈረንሳይኛ ቋንቋ መናገር የሚችሉ መሆን አለባቸው፡፡ በዘመቻ መልክ በዚህ የቋንቋ ክህሎት ላይ በመስራት ለውጥ ማምጣት ይቻላል፡፡ በተጨማሪም በየሆቴሎቹ የእንግዳ መስጫ ክፍል፤ የማረፊያ አዳራሾች---- የአገሪቱን የቱሪዝም መዳረሻዎች በተመለከተ መረጃ የሚሰጡ የተለያዩ ህትመቶች ተሟልተው መገኘት ይኖርባቸዋል፡፡ በጉዞና በአስጎብኝነት ስለሚሰሩ ተቋማት ግልፅ የሆኑ መረጃዎች ያስፈልጋሉ፡፡ በአጠቃላይ በአየር ማረፊያ፤ በትራንስፖርት ከዚያም በሆቴል አገልግሎቶች ማንኛውም ቱሪስት በሚያደርጋቸው የመጀመርያዎቹ 3 ሰዓታት ቆይታ በትኩረት መስራት የቱሪስቶችን ፍሰት  ለማሳደግ ወሳኝ ነው፡፡
በሌላ በኩል ከተለያዩ አገራት የሚመጡ ቱሪስቶችን በአግባቡ ማስተናገድ የሚቻለው ስለ ባህላቸው በቂ ዕውቀትና ግንዛቤ ሲኖር ነው፡፡ የተለያዩ አገራት መገለጫ የሚሆኑ ባህላዊ እሴቶች በጥናት ገምግሞና ለአገልግሎት አሰጣጥ መዘጋጀቱ ለቱሪስቶች የላቀ እርካታ የሚፈጥር መሆኑን ማወቅ ያስፈልጋል። ስለዚህም የቱሪዝም ባለድርሻ አካላት፣ የመንግስት ሰራተኞች፣ አስጎብኚ ድርጅቶች፣ የጉዞ ወኪሎች፣ የሆቴል ማናጀሮች፣ አስተናጋጆች በየአገራቱ ባህላዊ እሴቶች ዙሪያ በቂ ግንዛቤ ሊኖራቸው በሚያስችል ፖሊሲ መንቀሳቀስ ያስፈልጋል። ባህላዊ እሴቶችን ጠንቅቆ ከማወቅ  ባሻገር የቱሪዝም ዲፕሎማሲን ማጠናከርም ወሳኝ ነው፡፡ ከተለያዩ አገራት የቱሪዝም ውጤታማ ተመክሮዎችን ለመቅሰም የሚያስችሉ የተቀናጁ የግንኙነት  መረቦች መዘርጋት ያስፈልጋል። በተለይ በዳያስፖራው ተጠቅሞ መንቀሳቀስ ውጤታማ ያደርጋል፡፡ ትውልደ ኢትዮጵያውያን፣ የታሪክ ጉዳዮች ግንኙነት ያላቸው፣ የጥቁር ህዝብ ምሁራኖችና ታጋዮች፣ የፓን አፍሪካ አቀንቃኞች… የቱሪዝሙ ባለድርሻ አካል መሆን አለባቸው፡፡
በመጨረሻው  ምን የምትለው አለህ?
በእኔ በኩል ከኢትዮጵያ የቱሪዝም እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ በየክልሎች በመዘዋወር ባከናወንኳቸው ተግባራት ከተለያዩ የቱሪዝም ሃላፊዎች ጋር መልካም ግንኙነት ስለፈጠረልኝ፤  ወደፊትም ይህን መልካም ግንኙነት በሚያጠናክሩ የተለያዩ ስራዎች ላይ በመሳተፍና ድጋፍ በመስጠት ለመቀጠል እፈልጋለሁ። ለቀጣይ ትውልድ ተምሳሌት በሚሆኑ የተለያዩ የቱሪዝም እንቅስቃሴዎች ላይ የበኩሌን አስተዋፅኦ ማድረግ እንደምችል ሙሉ እምነት አለኝ፡፡ በተለያዩ የቱሪዝም ማስተዋወቂያ የህትመት ውጤቶች፣ በትርጉምና በአርትኦት ሥራዎች ለመሳተፍ፤ በቱሪዝሙ መስክ የሰው ሃይል በማደራጀትና የአቅም ግንባታ ዙርያ ስልጠናዎችን በመስጠት ማገልገል ነው ምኞቴ፡፡
ለምወዳት ኢትዮጵያ በምሰራው ሁሉም ነገር የላቀ ኩራት ይሰማኛል፡፡ በቀጣይ ግን ያለኝን እውቀት፤ ሙያ፤ የዳበረ ልምድ በመጠቀም በሚመለከተው የመንግስት አካል የስራ ፈቃድ ተሰጥቶኝ ወይም ተቀጥሬ የምሰራበት ሁኔታ እንዲፈጠር እፈልጋለሁ። በኢትዮጵያ ውስጥ ልሰራበት የሚያስችለኝ የስራ ፈቃድ ‹‹ዎርክ ፐርሚት›› እንዲሰጠኝ ማመልከቴ አይቀርም፡፡ በጎ ምላሽ እንደማገኝበትም ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ በሆቴልና የቱሪዝም አስተዳደር በርካታ ስራዎችን ማከናወን እችላለሁ። የተለያዩ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች በማዘጋጀት ማስተማር እችላለሁ። ልዩ ልዩ የማርኬቲንግ፤ የማስተዋወቅ፤ የፕሮጀክት እንቅስቃሴዎች ማካሄድም ይቻላል፡፡ ህጋዊ የስራ ፈቃድ የማገኝ ከሆነ ከመንግስትና ከግል የቱሪዝም ተቋማት ጋር በአጋርነት ከመስራት ባሻገር የራሴን ድርጅት በመክፈት ልሰራም አቅሙ አለኝ። በቱሪስት አስጎብኝነት፤ በጉዞ ወኪልነት፤ በተለያዩ የፕሮሞሽንና የማስታወቂያ ህትመት በፈረንሳይኛና እንግሊዘኛ ቋንቋ አስተርጓሚነት ተርጓሚነትና አስተማሪነት፤ በቱሪዝም ረገድ ዓለም አቀፋዊ የግንኙነት መረቦች በመዘርጋት፤ ወዘተ…  ብዙ መስራት ይቻላል፡፡

   1ኛ. ፍፁም የማላሸንፈውን ነገር እንድተው እንዲያደርገኝ
                 2ኛ. የማሸንፈውን ነገር ዳር እንዳደርስ ድፍረት እንዲሰጠኝ
                 3ኛ. በአንደኛውና በሁለተኛው መካከል ያለውን ልዩነት እንዳውቅ እንዲረዳኝ

     በጥንት ዘመን በህንድ አገር የሚነገር አንድ ዝነኛ አፈ - ታሪክ እንዲህ ይላል፡፡
ከሂማሊያ ተራራ ግርጌ በሚፈሰው በታወቀው የጋንጀስ ወንዝ ዙሪያ የሚኖሩ የተለያዩ ዓይነት ሰዎች ነበሩ ይባላል፡፡ ከልዩነታቸው ሁሉ በተለየ የሚያጨቃጭቃቸው የውሃ ሀብታቸው ነበር፡፡ ሁሉም ስለ ውሃቸው ጉዳይ ከመንደሩ ብልህ አዛውንት ፊት እየቀረቡ በየጊዜው ይከራከራሉ፡፡
“የእኛ ውሃ ከተራራ አለት መካከል የሚፈልቅ በመሆኑ ጥራት አለው፡፡ ከዚያ ሌላ በመጠጥም ቢሆን በማናቸውም አቅጣጫ ከሚፈሰው ውሃ ብዛት አለው፡፡ ስለዚህ ለጋንጀስ ወንዝ ትልቅ አስተዋፅኦ ያለን እኛ ነን፡፡” ይላሉ፡፡
ከሂማሊያ ተራራ በተቃራኒው አቅጣጫ የሚኖሩት ሰዎች ደግሞ፤
“የለም፤ የተሻለ ውሃ ያለን እኛ ነን፡፡ የእኛ ውሃ ብዙ ማዕድን ያለው፣ በጥንታዊነቱም የታወቀ፣ የበለፀገ ሀብት ያለው፣ ዙሪያ ገባውን እያራሰ፣ የሜዳውን መስክ እያረሰረሰና መስኩን እያለመለመ፣ ለከብት ግጦሽ ጭምር የሚያገለግል ነው፡፡ ዋና ተጠቃሚ መሆን ያለብን እኛ ነን” ሲሉ ይከራከራሉ፡፡
ከሁለቱ ወገኖች የሚለዩት ከሂማሊያ ጀርባ የሚኖሩት ሶስተኛዎቹ ሰዎች፤
“የእኛን ውሃ የሚያክል በፍፁም የለም! ምክንያቱም የኛ ውሃ ፀበልነት አለው፡፡ ቅዱስ ነው፡፡ ስንቱ ቢስ - ገላ፣ ስንቱ ሽባ፣ ስንቱ በሽተኛ የሚፈወስበት ነው፡፡ አገር የሚድነው በእኛ ውሃ ነው፡፡ ስለዚህም የተሻለ አስተዋፅኦ ስላለን የተሻለ ጥቅም ይገባናል” ይላሉ፡፡
በአራተኛ ወገን ቆመው የሚከራከሩትና ከሰሜን ምዕራብ አቅጣጫ የሚፈሰው ወንዝ ዙሪያ የሚኖሩት ሰዎች በበኩላቸው፤
“ከማናችሁም የተሻለ ገባር፣ ወንዝ ያለን እኛ ነን፡፡ ለምን ብትሉ የእኛ ውሃ ገስጋሽ ነው፡፡ ኃይል አለው፡፡ ትልቁን የጋንጀስ ወንዝ እየገፋ፣ አቅም እየሰጠ፣ የሚያንቀሳቅሰቀው የእኛ ውሃ ነው!” አሉ፡፡
እንግዲህ የአራቱም ወገኖች ክርክር ዳኝነት እንዲያገኝ የሚጠበቀው ከመንደሮቹ አባት ከብልሁ አዛውንት ነው፡፡ አንዳቸው በጥራት አንዳቸው በማዕድን ይዞታ፣ አንዳቸው በፈዋሽነት፣ አንዳቸው በፍጥነትና በኃይል የተሻልን ነን በሚል የተሻለ ጥቅም ጠየቁ፡፡
የመንደሩ ብልህ አዛውንት ሁሉንም ካዳመጡ በኋላ፣ ሰፈራቸው ላይ ወጥተው፤
“ኑ ተከተሉኝ” አሉና ከመንደሩ ርቀው የጋንጀስ ወንዝን ተከትለው ጋለቡ፡፡ አራቱም ወገኖች እየጋለቡ ተከተሉ፡፡ መንደሮቹን ወደ ኋላ እየተዉ ፍፁም ከማይታዩበት ሌላ አካባቢ ሲደርሱ አዛውንቱ ወረዱና፤
“ይሄ ማን የሚባለው ወንዝ ነው?” ሲሉ አራቱንም ወገኖች ጠየቁ፡፡
“የጋጀስ ወንዝ ነዋ!” ሲሉ መለሱ፤ ሁሉም በአንድ ድምፅ፡፡
አዛውንቱም፤ “መልካም፡፡ በሉ አሁን እያንዳንዳችሁ የየራሳችሁን መንደር ውሃ ከዚህ ወንዝ ውስጥ አውጡና አሳዩኝ!” ሲሉ ጠየቁ፡፡ አንዳቸውም የኔ ነው የሚሉትን ውሃ ሊያሳዩ አልቻሉም፡፡ የሁሉም መንደር ውሃ አንድ ጋንጀስ ሆኗል፡፡
*         *       *
ሁሉም ገባር ወንዞች ተቀላቅለው ወደ አንድ ትልቅ ወንዝ ይፈስሳሉ፡፡ ማናቸውንም ከሌላው መለየት የማይቻልበት ደረጃም ይደርሳሉ፡፡ የእኔ መንደር ውሃ ከሌላው መንደር ውሃ ይበልጣል የሚለውን አስተሳሰብ የጋንጀስ ወንዝ ይዞት ሄዷል፡፡ ሁላችንም ስለ ትልቅ ስዕል ማሰብ ስንችል አገር እናድናለን፡፡ ትልቁ የጋንጀስ ወንዝ ትናንሾችን ገባር ወንዞች ሁሉ ጠቅልሎ፣ አንድ ወንዝ ሆኖ መፍሰስ፣ የአንድን ትልቅ አገር ህልውና ምስል ይሰራልናል፡፡
ፍትሕም፣ ዲሞክራሲም፣ መልካም አስተዳደርም፣ የፖለቲካ ጥራትም፣ ንፁህ እጅም አንድ ላይ በአግባቡ ሲፈስሱ፣ አገር የመንቀሳቀስ ኃይልና አቅም ታገኛለች፡፡ የእኔ አስተዋፅኦ ይበልጣል ብሎ ተገዳድቦ መለያየት የአንድነት ፀር ነው፡፡ አገርን ይሸረሽራል፡፡ አቅምን ያኮስሳል፡፡
ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን፤
“የአበሻ መኪና አነዳድ በሌላው መንገድ
መገድገድ፣ የአበሻ ንግድ የሌላውን ንግድ ማሽመድመድ›› የሚለን፤ ይሄንኑ ሀቅ ለማፀህየት ነው!
ተነጣጥለን ልዩነትን በማስፋት የትም አንደርስም፡፡ ኅብር ልንፈጥር የምንችለው ዜማችን አንድ ሲሆን ነው፡፡ ፍቅራችን ከልብ ሲሆን ነው፡፡ ከልብ መደማመጥ ስንችል ነው፡፡ ልዩነት ቢኖረን እንኳን በሠለጠነ ጠረጴዛ ዙሪያ መፍታት አሊያም ተከባብሮ መቀመጥ ስንችል ነው፡፡ ለዚህ ቁልፉ በመቻቻል ማመንና በተግባር ማሳየት መቻል ነው፡፡ ትዕግሥት ፍርሃት አለመሆኑን የምናውቀውን ያህል፤ አጉል ድፍረትና አጉራ-ዘለል ፖለቲከኝነት ወንዝ እንደማያሻግር ማወቅ ያስፈልጋል…
ዛሬ ‹‹በቆሼ ሠፈር›› የደረሰውን አሰቃቂ አደጋ በሐዘንና በቁጭት እናስበዋለን፡፡ አደጋን አስቀድመን ለማሰብ እንችል ዘንድ የህዝብን ፍርሃትና ሥጋት አለመናቅ ዋና ነገር ነው፡፡ ቅን ልቦና ቢኖረን መልካም ነው፡፡ የሕዝብን ደግ ማሰብ፣ የልብ ትርታውን ለማዳመጥ፣ ኑሮውን መመርመር ተገቢ ነገር ነው። ለቅድመ ጥንቃቄ ይጠቅመናል፡፡ አደጋ ከደረሰም በኋላ በኅብረት መረባረብን ህዝብን ለመታደግ አቅምና ልብን መስጠትን፤ ህዝብን ማስተባበርን ሆነኝ ብሎ ማሰብ፣ ከዚያም የሚገኘውን ትምህርት ማጤን፣ አፋጣኝ መፍትሔ ለማግኘትም ሳይነጣጠሉ መጣር ያሻል፡፡ የአገር ጉዳይ ነውና አገር አደጋውን መቋቋሚያ ማሽኖችን ማቅረብ አለባት፡፡ የክሬኖችንና የመቆፈሪያዎችን እጦት መቋቋም ካቃተን የአደጋ አደጋ አለብን፡፡ ወይ ህዝብን ለመርዳት ፈቃደኝነት ማጣት አለ፡፡ አሊያም የችግራችን ጥልቀት አሰቃቂነት እጅግ አሳሳቢ ደረጃ ደርሷል ማለት ነው፡፡ ለወገን መድረስ ይጠበቅብናል፡፡ ጊዜ እየመረጥን ሳይሆን ሁልጊዜ!! ተከታዩ ጉዳይ የተጎዳውን ህዝብ ማቋቋምና ሌላ ቦታ ለማስፈር ምን አርምጃ እንውሰድ የሚለው ነው፡፡ የሚመለከተው ክፍል ይህን ያስብበታል ብለን እንገምታለን፡፡ አደጋው ድንገተኛና በችግር ላይ ችግር የፈጠረ መሆኑ አያጠያይቅም፡፡ አገራችን አንዴ በጎርፍ አንዴ በድርቅ፣ አሁን ደግሞ በናዳ፣ መጠቃቷን እናያለን፤ ችግር ፈቺ ዘዴንና ቅድመ ዕቅድን  የማዘጋጀትን ሥራ አቅም በፈቀደ መሥራት አለብን፡፡ አገራችን የችግር ቋት መሆኗን ደጋግመን አውስተናል፡፡ የፖለቲካውን፣ ኢኮኖሚውንና የማኅበራዊውን ድርብርብ ችግር በቅደም ተከተል የምንፈታበትን ዘዴ ካላዘጋጀን ወደ ባሰ ማጥ ልንገባ እንችላለን፡፡ አቅምን አግዝፎ ማየትም፣ ከልኩ በታች አቀጭጮ ማየትም አደጋ ነው፡፡ ስለዚህ ፀሎተኛው እንዳለው፤ አምላክን የምለምነው ሶስት ነገሮች፡-
1ኛ/ ፍፁም የማላሸንፈውን ነገር እንድተው እንዲያደርገኝ
2ኛ/ የማሸንፈውን ነገር ዳር እንዳደርስ ድፍረት እንዲሰጠኝ
3ኛ/ በአንደኛውና በሁለተኛው መካከል ያለውን ልዩነት እንዳውቅ እንዲረዳኝ ነው ማለት ብልህነት ነው፡፡
አደጋ ለደረሰባቸው ሁሉ ፅናቱን እንዲሰጣቸው እንመኛለን!!

Saturday, 18 March 2017 15:06

ከልብ አዝነናል!!

“ቆሼ” እየተባለ በሚጠራው ሥፍራ በደረሰው አደጋ በርካታ ወገኖቻችን ለህልፈት በመዳረጋቸው የተሰማንን ጥልቅ ሃዘን እየገለፅን፣ ለሟች ቤተሰቦችና ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ መፅናናትን እንመኛለን፡፡ በተመሳሳይ በጋምቤላ ክልል፣ የደቡብ ሱዳን የሙርሌ ታጣቂዎች በፈፀሙት ጥቃት ህይወታቸውን ላጡ ኢትዮጵያውያን ጥልቅ ሀዘናችንን እየገለፅን፣ ለቤተሰቦቻቸው ፅናቱን እንመኛለን!! ታፍነው የተወሰዱትን 43 ህፃናትን
ለማስመለስም መንግስት የማያወላውል ቁርጠኝነቱን እንደሚያሳይም ተስፋ እናደርጋለን፡፡ ለአገራችን መልካሙን ዘመን ያምጣልን!!
                   አዲስ አድማስ - የእርስዎና የቤተሰብዎ

Monday, 20 March 2017 00:00

ማረሚያ

    ባለፈው ሳምንት የጋዜጣው ዕትም “በማዕተብ ጉዳይ ከመምህሩ ጋር የተጋጨው ተማሪ ራሱን አጠፋ” በሚል ርዕስ በወጣው ዜና ላይ ተማሪው የጅማ ዩኒቨርሲቲ የመምህራን ኮሌጅ ተማሪ እንደሆነ የተገለፀው በስህተት ሲሆን ተማሪው በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ትምህርት ቢሮ በሚተዳደር “የጅማ መምህራን ኮሌጅ” ይማር የነበረ መሆኑን ለመግለፅ እንወዳለን፡፡ ለተፈጠረው ስህተት ውድ አንባቢያንንና የጅማ ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰብን ልባዊ ይቅርታ እንጠይቃለን፡፡

    በአዲስ አበባ፣ የካ ክፍለ ከተማ፣ ወረዳ 12፣ ልዩ ስሙ አባዶ ቁጥር 1 እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የተሠራችው የደብረ ልዕልና ቅድስት አርሴማ  ቤተ ክርስቲያን፣ ሕገ ወጥ ግንባታ በሚል በደንብ ማስከበር ጽ/ቤቱ በከፊል የፈረሰባቸው መኾኑን የገለጹ ካህናትና ምእመናን፣ የድረሱልን ጥሪ አሰሙ፡፡
በከተማው መልሶ ማልማት ወደ አካባቢው የሔዱት ነዋሪዎቹ፣ ሥርዓተ አምልኰ የሚፈጽሙበት ቤተ ክርስቲያን ተቸግረው መቆየታቸውንና ከአራት ወራት በፊት፣ ከግለሰቦች በስጦታ ባገኙት ቤትና ቦታ ላይ በሀገረ ስብከቱ ፈቃድ በቅድስት አርሴማ ስም ቤተ ክርስቲያን ተክለውና አስባርከው በመገልገል ላይ እንደነበሩ ካህናቱና ምእመናኑ ገልጸዋል፡፡500 ካሬ ሜትር ስፋትና 30 ቆርቆሮ ቤት ያለውን ቦታ ለመኖርያና ለእርሻ ይገለገሉበት የነበሩት ግለሰቦች፣ በስማቸው ተመዝግቦ ግብር ይገብሩበት እንደነበርና ሕጋዊ ባለይዞታዎች ለመኾናቸው የሚያረጋግጥ ማስረጃ እንዳላቸው ካህናቱና ምእመናኑ ጠቅሰዋል፤ ለቤተ ክርስቲያን መሥሪያ በስጦታ ሲያበረክቱም፣ በውል ተቀባይነት የተረከቡት፣ በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት የተወከሉ የመሥራች ኮሚቴው ካህናት መኾናቸውን አስረድተዋል፡፡
የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤትም፣ የነዋሪዎቹን ማመልከቻና በአባሪነት ያቀረቧቸውን ማስረጃዎች መሠረት በማድረግ፣ ቤተ ክርስቲያን ለማነጽ ይቻል ዘንድ የወረዳው አስተዳደር ጽ/ቤትና የሚመለከታቸው አካላት አስፈላጊውን ትብብር እንዲያደርጉ በደብዳቤ መጠየቁን አውስተዋል፡፡
ኾኖም፥ የወረዳው አስተዳደር፣ ከኹለት ሳምንት በላይ አንዳችም ምላሽ ሳይሰጥ ቆይቷል፤ ያሉት ካህናቱና ምእመናኑ፣ ዝምታውን እንደ ይኹንታ በመቁጠር፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የታዘዘላቸውን ጽላት አስገብተው መንፈሳዊ አገልግሎት መጀመራቸውን ገልጸዋል፤ የግለሰብን ቤት በቀጥታ
ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መጠቀም ስለሚከብድም፣ ዲዛየኑንና ቆርቆሮውን መቀየራቸውን ጠቅሰዋል፡፡
መንፈሳዊ አገልግሎታቸውን በማከናወን ላይ ሳሉም፣ የወረዳው የደንብ ማስከበር ጽ/ቤት፣ የንብረት ማስቀመጫ ኮንቴይነሩ ብቻ ሲቀር ሌላውን አፍርሶ ንብረቱን ወደ ፖሊስ ጣቢያ ማስገባቱን፣ ስምንት ካህናትም መደብደባቸውንና የመሥራች ኮሚቴው አባላትም ለአራት ቀናት ታስረው
እንደነበር ነዋሪዎቹ ተናግረዋል፡፡የታሰሩት ከተፈቱ በኋላ፣ ጉዳዩ በሕግ ታይቶ ባለመብት መኾናቸው እስኪረጋገጥ፣ ያለው ንብረት ቁልፉ ተከብሮ እንዲቀመጥ በፍርድ ቤት የእግድ
ትእዛዝ ቢያስወጡም፣ አጥሩና ምእመናኑ ለጥላ የሚገለገሉበት ሸራ፥ በደንብ ማስከበር ጽ/ቤቱ መፍረሱን፤ ዶማ፣ አካፋ፣ ድጅኖ የመሳሰሉ መሣሪያዎችም መወሰዳቸውን፤ ዘወትርም ዛቻና ማስፈራሪያ እየደረሰባቸው እንዳለ ዘርዝረዋል፡፡“ሕገ ወጥ ብንኾን፣ በሕግ እንጠየቃለን እንጂ ኢሰብአዊ በኾነ ኹኔታ ሊደበድቡንና ዘወትር እያስፈራሩን ሊቀጥሉ አይችሉም፤” ያሉት አንድ ካህን፣ መንግሥት ስለ እምነት ነጻነት ከሚናገረው አንጻር፣ “እነዚኽ ሰዎች እነማን እንደኾኑ ለመናገር እንቸገራለን፤” ሲሉ ምሬታቸውን ገልጸዋል፡፡በአኹኑ ወቅት በመቅደስነት የሚገለገሉበት፣ የንብረት ማስቀመጫ ኮንቴነር መኾኑን ጠቅሰው፣ ለአራት ወራት የተቀደሰበት ቤተ ክርስቲያን እንዳይፈርስና ተረጋግተው ማገልገል እንዲችሉ፣ ለክፍለ ከተማ አስተዳደሩ የደንብ ማስከበር ጽ/ቤት ትእዛዝ እንዲሰጥላቸው፣ ለከንቲባው ጽ/ቤት መጠየቃቸውን አመልክተዋል፤ ጉዳዩ በፍ/ቤት ለመጋቢት 27 ለውሳኔ መቀጠሩንም አስታውቀዋል፡፡   ስለጉዳዩ የደንብ ማስከበር ጽ/ቤቱን አስተያየት በስልክ ለማግኘት ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ፣ ጥሪ ባለመመለሱ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡





    አዲስ ኢንተርናሽናል ባንክ ከትናንት በስቲያ በሸራተን ሆቴል በላኪነት፣ በአስጎብኚነት፣ በማማከርና በገንዘብ አስቀማጭነት የላቀ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ደንበኞቹ የሰርተፍኬትና በሦስት ደረጃ የዋንጫ ሽልማት ሰጠ፡፡
የፕላቲኒየም ተሸላሚ የሆኑት ድርጅቶች ካቤ ፒኤልሲ፣ የይርጋጨፌ የገበሬዎች ኅብረት ሥራ ማኅበራት ዩኒየን፣ ሐግቤስ ፒኤልሲና ግሪንላንድ ፒኤልሲ ሲሆኑ ሌሎችም የወርቅና የብር ዋንጫ ተሸልመዋል፡፡
አዲስ ኢንተርናሽናል ባንክ በአብዛኛው በኅብረት ስራ ማህበራት፣ እድሮች፣ አነስተኛ የብድር አቅራቢ ተቋማትና ግለሰቦች የተመሰረተ ሲሆን የባለአክሲዮኖቹም ቁጥር በቀጥታና በተዘዋዋሪ ከ300,000 በላይ ይሆናል፡፡
ባንኩ ከጊዜ ወደ ጊዜ የቅርንጫፍ ስርጭቱን በአዲስ አበባና በክልል ከተሞች ለንግድ ስራ ምቹ በሆኑ ቦታዎች እያስፋፋ ሲሆን ሞባይልና ኢንተርኔት አገልግሎት ጨምሮ፤ ሁሉንም ቅርንጫፎቹን በመረጃ መረብ በማገናኘት ቀልጣፋ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑ ታውቋል፡፡



የዘንድሮ የአድዋ በዓልን አስመልክቶ ለአራተኛ ጊዜ የተካሔደው ከአዲስ አበባ አድዋ ‹‹ጉዞ አድዋ 4›› የእግር ጉዞ ከጥር 9 ጀምሮ የካቲት 23 ቀን 2009 ዓ.ም በደማቅ አቀባበል በአድዋ ከተማ መጠናቀቁ ይታወቃል፡፡ የእግር ጉዞውን በስኬት ያጠናቀቁ ተጓዦችን በደማቅ ስነስርዓት ለመቀበል
የፊታችን ሰኞ መጋቢት 11 ቀን ከምሽቱ 11፡45 ጀምሮ በአምስት ክሎ ብሔራዊ መዚየም ቅጥር ግቢ በሚገኘው ሉሲ ሬስቶራንት አዳራሽ፣ ልዩ ልዩ ኪናዊ ዝግጅቶችና የእራት ምሽት ተዘጋጅቷል፡፡
ለዘንድሮው ጉዞ አድዋ መሳካትና በሀገር አቀፍ ደረጃ የዓድዋ ክብረ በዓል ደማቅ እንዲሆን የላቀ ሚና ያበረከቱ የሚዲያ ተቋማትና ግለሰቦች የክብር አቀባበሉ ሥነስርዓት ተካፋይ ይሆናሉ ተብሏል፡፡
‹‹ጉዞ ዓድዋ›› በቀጣይ ዓመታት የአፍሪካ ተጓዦችን በእግር ጉዞው ለማሳተፍ ያለውን እቅድም በይፋ የሚገልጽበት ምሽት እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡

 

  የቀድሞ የህፃናት አምባ ውስጥ አድገው በተለያዩ የስራ መስክ በተሠማሩ ግለሠቦች የተቋቋመው ‹‹ትምህርት ለተቸገሩ በጎ አድራጎት ማህበር›› መጋቢት 10 ቀን 2009 ዓ.ም የገቢ ማሠባሠቢያ ፕሮግራም ያካሂዳል፡፡
ከ3 መቶ በላይ የትምህርት እድል ማግኘት ያልቻሉ ህፃናትን በኮተቤ ኪዳነምህርት ቤተ ክርስቲያን አካባቢ በከፈተው ትምህርት ቤት በማስተማር የሚታወቀው ማህበሩ፤ በአሁኑ ወቅት ይህን በጎ ተግባር ለማከናወን የአቅም ውስንነት ስላጋጠመው የእርዳታ ማሠባሠቢያ መርሃ ግብር ለማዘጋጀት መገደዱን አስታውቋል።
በዚህም መሰረት መጋቢት 10 ቀን 2009 ዓ.ም ከላምበረት አዲሱ መናኸሪያ ተነስቶ እስከ ኮተቤ ኪዳነ ምህረት ቤተክርስቲያን የ3.5 ኪሎ ሜትር የእግር ጉዞ በማዘጋጀትና የሙዚቃ ዝግጅትን አካቶ የገቢ ማሠባሠቢያ ሰፊ ፕሮግራም እንደሚያደርግ አስታወቆ፤ በእለቱ ድጋፍ እንዲደረግለት ጥሪ አድርጓል፡፡

 በጅማ ዩኒቨርሲቲ መምህራን ኮሌጅ የ2ኛ ዓመት የእንግሊዝኛ ቋንቋ ተማሪ፣ የሆነው ወጣት በአንገት ማዕተብ ጉዳይ ከመምህሩ ጋር ተጋጭቶ “የትምህርት ውጤቴ ተበላሸ” በሚል ራሱን አጠፋ፡፡
ተስፋዬ ገመዳ የተባለው ተማሪ የስነ ልቦና ሳይንስ መምህሩ በቡድን ያዘዙትን አሳይመንት ስራ አዘጋጅቶ በመድረክ ላይ ሊያቀርብ ሲል መምህሩ፣ “በአንገትህ ላይ ያደረከውን ማተብ ወይ አውልቅ ወይም ሸፍነው” ሲሉት ተማሪው፤ “ይህ የእምነቴ መገለጫ ነው፤ ያዘዙኝን ማድረግ አልችልም” የሚል ምላሽ እንደሰጣቸውና መምህሩም “ያዘዝኩህን ማድረግ ካልቻልክ የሰራኸውን ማቅረብ አትችልም” በማለታቸው ስራውን ሳያቀርብ መቅረቱንና ከመድረኩ ወርዶ በእጁ የያዘውን የቡድን  ስራ ሪፖርት በንዴት ቀዳዶ መቀመጡን የአይን እማኞች አስታውሰዋል፡፡ በወቅቱ ተማሪው ክፍለ ጊዜውን አቋርጦ ከክፍሉ መውጣቱንና ተመልሶ  ሊገባ ሲል መምህሩ አትገባም ብለው እንደከለከሉትና፣ ተማሪውም ስሜታዊ ሆኖ ከመምህሩ ጋር ለፀብ መጋበዙን፣ ተማሪዎችም በመሃል ገብተው እንደገላገሏቸውና የአካዳሚክ ዲኑ በቦታው ተገኝተው ስለተፈጠረው ችግር ተማሪዎችን በመጠየቅ፣ ፀቡን ማረጋጋታቸውን ተማሪዎች ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡
በሌላ ቀን እንደተለመደው ተማሪው የስነልቦና ክፍለ ጊዜ ትምህርቱን ለመከታተል ወደ ክፍል ሲገባ መምህሩ በድጋሚ ከክፍል እንዳስወጡት፣ ተማሪውም ለአካዳሚክ ዲኑ አቤቱታ ማቅረቡንና ዲኑም የትምህርቱ የመጨረሻ ክፍል ጊዜ ስለሆነ ‹‹በቃ ተወው በውጤትህ ላይ ምንም ለውጥ አያመጣም›› ብለው አረጋግተው እንደሸኙት፣ የተማሪው የቅርብ ጓደኞች ገልፀዋል፡፡
በኋላም ፈተና እንዲወስድ የተፈቀደለት ሲሆን የተለጠፈውን የፈተና ውጤት ሲመለከት ግን “No Grade” (ምንም ውጤት የለም) የሚል ስለነበር ወዲያው በንዴት ወደ ተከራየበት ቤት በማምራት የዚያኑ እለት ራሱን ግቢ ውስጥ ባለ የማንጎ ዛፍ ላይ  ሰቅሎ ማጥፋቱን የቅርብ ጓደኞቹ ገልፀዋል፡፡
ፖሊስና የአካባቢው ህብረተሰብ በቦታው ደርሶ ከተሰቀለበት ሲያወርዱት ነፍሡ ከስጋው  እንዳልተላቀቀችና ወደ ሆስፒታል በመሄድ ላይ ሣለ ህይወቱ ማለፉን የጠቆሙት ምንጮች፤ የቀብር ሥነስርዓቱም ከትናንት በስቲያ በትውልድ አካባቢው በሰሜን ምዕራብ ሸዋ፣ ደገሞ ወረዳ መፈፀሙን ለማወቅ ተችሏል፡፡
አስከሬኑን ለቤተሰብ ያደረሱት መርማሪ ፖሊስ ዮሐንስ መገርሳ፤ ተማሪው ከመምህሩ ጋር በመጣላቱ ራሱን  እንዳጠፋ ጥርጣሬ መኖሩንና የሆስፒታል የምርመራ ውጤት በማስረጃነት እየተጠበቀ መሆኑን ጠቁመው፣ ጉዳዩ ገና በመጣራት ላይ ነው ብለዋል - ለአዲስ አድማስ በሰጡት ማብራሪያ፡፡

 ከቻይና ስመ-ጥር የጫማ አምራች ኩባንያዎች አንዱ የሆነውና ከአምስት አመታት በፊት በኢትዮጵያ ፋብሪካውን ከፍቶ የማምረት ስራ የጀመረው ሁጂያን ግሩፕ፤ ኢንቨስትመንቱን ለማስፋፋትና ለ100 ሺ ሰዎች ተጨማሪ የስራ ዕድል ለመፍጠር ማቀዱን አስታወቀ፡፡
ሁጂያን ግሩፕ ለ6 ሺህ ያህል ኢትዮጵያውያን ዜጎች የስራ ዕድል መፍጠሩንና ለአገሪቱ የውጭ ምንዛሬ በማስገኘት ረገድ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ያስታወሱት የኩባንያው ፕሬዚዳንት ዣንግ ሁዋሮንግ፤ 100 ሺህ ያህል አዳዲስ የስራ ዕድሎችን የመፍጠርና ካፒታሉን ወደ 10 ቢሊዮን ዶላር የማሳደግ ዕቅድ እንዳለው መግለጻቸውን ፒፕልስ ዴይሊ ድረገጽ ዘግቧል፡፡
ኩባንያው በኢትዮጵያ በከፈተው ፋብሪካ እያመረተ ለውጭ ለገበያ የሚያቀርባቸው የጫማ ምርቶች፣ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ልጅ የሆነቺው ኢቫንካ ትራምፕ ያቋቋመቺውን ኢፖኒመስ የተባለ ኩባንያ ጨምሮ በበርካታ የአውሮፓ አገራት ኩባንያዎች ዘንድ ተወዳጅነት ማትረፋቸውንም ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል፡፡