Administrator

Administrator

Saturday, 25 March 2017 12:42

“የቡና ቤት ሥዕሎችና …”

 አንድ ቡና ቤት ውስጥ ግድግዳው ላይ የተሣለ ነው፡፡ ሰውዬው በአንበሳው ላይ ይነጣጥራል። በሰውዬውና በአንበሳው መካከል ጅረት አለ። አዳኙን እግሩ ቀጥ እንዳለ ስታዩት ሣሩ ላይ ተኝቷል ብላችሁ ታስባላችሁ፡፡ ነገር ግን መሆን አለበት ብላችሁ ስለምትገምቱ ነው እንጂ ሥዕሉ ላይ የሚታየው በሣሩ ላይ ሲንሳፈፍ ነው፡፡
እሺ ብሎ አይዞርላችሁም እንጂ ግድግዳውን ዞር ብታደርጉት ደግሞ ቆሞ እሚተኩስ ይመስላችኋል። አንበሳው በተዝናና ሁኔታ ሰውዬውን ትኩር ብሎ ያየዋል። አስተያየቱን ለመግለጽ ያስቸግራል፡፡ ብቻ፣ ‹‹እውነት አሁን ልትተኩስ ነው እስቲ ወንድ!›› የሚል ይመስላል፡፡
የሥዕሉ ምጣኔ ነገር አይወራም፡፡ የፊት እግሮቹ እኩል አይደሉም፡፡ አንዱ ወፍራም አንዱ ቀጭን ነው፡፡ የጅራቱን ማጠር ስታዩ፣ ሥዕሉ ሲሣል ግድግድጋው ጠባብ ነበር እንዴ ማለታችሁ አይቀርም፡፡ የወገቡም ቅጥነት፣ ‹‹ሽንጧ ስምንት ቁጥር›› የሚለውን ዘፈን ያስታውሳችኋል፡፡ የቅርበት-ርቀቱ ሚዛን እንዳልተጠበቀ በግልጽ ይታያል። ለምሳሌ ጠመንጃው ከሰውዬው በልጦ ጅረቱን አቋርጦ አንበሳው አፍንጫ ሊደርስ ትንሽ ቀርቶታል። ከወዲያ ማዶ ያለው ጋራ ደግሞ አንበሳው ጀርባ ላይ ያረፈ ይመስላል፡፡ ከሁሉም ይልቅ የሚገርመው አውሬው ጥቂት እንኳ እንደ መዝለል ወይም እንደ መሸሽ ሳይል በኩራት ዝም ብሎ አዳኙን ማስተዋሉ ነው፡፡ ይኸን ሥዕል ሳይ የአንዳንድ አርበኞች ሥዕል ትዝ አለኝ፡፡
ወረቀቱ ስለማይበቃ ነው እንዳይሉን እንጂ የአርበኛው ጠመንጃ የጣልያኑን ዓይን እየወጋ፣ ‹‹ደጃች እገሌ ጠላት ላይ ሲያነጣጥሩ›› የሚል ከሥሩ እየተለጠፈበት፣ እንደ እንቁጣጣሽ አበባ እየዞረ ሲሸጥ፣ የእነ አብየ ገብረ መንፈንስ ቅዱስ፣ የቅዱሳን፣ የሰማዕታት፣ ያ ያ ሁሉ ታየኝ፡፡›› ታዲያ አሁን እዚህ ለምናነሣቸው መሰረቱ እነሱ ይመስሉኛል፡፡ ጥንት ከምዕተ ዓመታት በፊት የተሣሉትን ግን ለጥናት ሊጠቅሙ ስለሚችሉ ለታሪክና ቅርስ ተመራማሪዎች ቢተው ጥሩ ነው፡፡
ሌላው ያየሁት የፋሲል ግንብ ነው፡፡ ይኸ ሥዕል በብዛት በየቦታው ይታያል፡፡ አሣሣሉ አንድ ይምሰል እንጂ አጠቃላይ መልኩ የተለያየ ነው። አጥር ያለው፣ አጥር የሌለው፣ ዛፍ ያለው ዛፍ የሌለው፣ በጽጌረዳና በሀረግ ያጌጠ፣ በለምለም ሣር ያሸበረቀ፡፡ የአንዳንዱ ጥላ አጣጣል ፍጹም ቅጥ ያጣ ከመሆኑ የተነሣ ፀሐይዋ ሁለት የሆነች ሊመስላችሁ ይችላል፡፡ አንዳንዱ ከበረንዳው በታች ዘንባባ፣ ባሕር ዛፍ፣ ጥድ፣ በያይነቱ በሰልፍ ይተከልበታል፡፡ ምን ያህል እውነት እንደሆነ አላውቅም እንጂ ፓፓያ የተሣለበትም አለ ሲባል ሰምቻለሁ፡፡
የግንቡ የአካባቢ ሁኔታ ብቻ ሳይሆን፣ ቀለሙም ብዙ ዓይነት ነው፡፡ ቢጫ፣ ሰማያዊ፣ ሮዝ፡፡ የአራት መቶ ዓመት ህንፃ በፒያሳ ቀለም መታደሱ እንኳን አይከፋም፡፡ እኔን በጣም ያስገረመኝ ግን፣ ከግንቡ ፊት ለፊት፣ ከቤተ መንግሥቱ ፊት ለፊት አንዲት ሹርባ የተሠራች የሀገር ልብስ የለበሰች ውብ ወይዘሮ፤ ጃንጥላዋን ከፍ አርጋ ይዛ ገበያ አዳራሽ እምትሄድ ይመስል በቄንጥ ስትራመድ የሚያሳየው ሥዕል ነው፡፡ እስቲ ሴትየዋ እዚያ ምን ታደርጋለች? ላልጠፋ ግድግዳ … ለብቻዋ መሳልስ ይቻል የለም!
በተለይ የፋሲል ግንብን፣ የአክሱም ሐውልትን፣ ጢስ ዐባይን፣ ላሊበላን የሚሥሉ ሰዎች፣ ባዶ ቦታ ለምን ባዶውን ይቅር እያሉ ነው መሰለኝ፤ ደስ ያላቸውን ነገር ይጨምራሉ፡፡ ባዶ ቦታ ማስፈለግ አለማስፈለጉን ሳያስተውሉ፡፡ ለምሳሌ፣ ወፎችፐ ከሩቅ እየበረሩ ሲመጡ እንዲያውም ሰማይ ካለ ወፎች በግድ ይኖራሉ፡፡ ወንዝ ወይም ኩሬ ከተነሳ ዳክዬዎች ሲዋኙ መታየት አለባቸው፡፡ ዛፍ ደግሞ ጦጣ ከሌለችበት ዛፍ ሊሆን አይችልም። ሣሩም ሁልጊዜ አረንጓዴ ነው፡፡ ምናልባት ለዚህ የሚገፋፋቸው የኢትዮጵያ ልምላሜ ይሆን? በአጠቃላይ የቡና ቤት ሠዓሊያዎች ትልቅ ድክመት ዝምድና ወይም ግንኙነት የሌላቸውን ነገሮች ጎን ለጎን ማስቀመጣቸው ነው፡፡ ማን ያውቃል፣. ከፍ ብሎ የተጠቀሰችዋ ሴትዮ ሲገርመን፣ ላሊበላ ቤተክርስቲያን ላይ ጂንስና ቢትልስ ለብሶ ኳስ የሚያነጥር ልጅ እንድ ቀን እናይ ይሆናል፡፡
(ከደራሲ መስፍን ሀብተማርያም
“የቡና ቤት ሥዕሎች እና ሌሎችም ወጎች”
መፅሃፍ ላይ የተቀነጨበ)

Saturday, 25 March 2017 12:38

የክብር ዶክትሬት ጥያቄ?!

  አንድ ባለጸጋ በአካባቢያቸው ወደሚገኝ አንድ ኮሌጅ ጎራ ይሉና ለተቋሙ 1ሚ.ብር ለመለገስ እንደሚሹ ይናገራሉ፡፡ “ነገር ግን በአንድ ቅድመ-ሁኔታ ነው÷ ይኸውም የክብር ዶክትሬት የሚሰጠኝ ከሆነ ነው” ይላሉ፡፡
የኮሌጁ ፕሬዚዳንትም፤ “ታዲያ ምን ችግር አለ፤ ይሰጥዎታላ” ይላቸዋል፡፡
 “የክብር ዶክትሬቱ ግን ለአህያዬ ነው” አሉ፤ ባለጸጋው፡፡
ፕሬዚዳንቱ በድንጋጤና በአግራሞት መሃል ሆኖ፤ “ለአህያዬ?” ሲል ጠየቃቸው፡፡
ባለጸጋውም፤ “አዎ--- አህያዬ ለብዙ ዓመታት እኔን ተሸክማ ከቦታ ቦታ በመውሰድ ከባድ ውለታ አድርጋልኛለች፡፡ ለዚህም የትራንስፖርት የክብር ዶክትሬት እንዲሰጣት እሻለሁ; በማለት ኮስተር ብለው አስረዱ፡፡
“ግን እኮ---- ኮሌጃችን ለአህያ የክብር ዶክትሬት ሰጥቶ አያውቅም” አለ ፕሬዚዳንቱ፡፡
“እንግዲያውስ ገንዘቡን ለሌላ ተቋም እለግሰዋለሁ” አሉና ከመቀመጫቸው ተነሱ-ባለሃብቱ፡፡
ዓይኔ እያየ 1ሚ.ብር ሊያመልጠኝ ነው ብሎ ያሰበው ፕሬዚዳንት፤ “ቆይ እስቲ ከኮሌጁ ቦርድ ጋር ልማከርበት” ሲል ጥቂት ጊዜ እንዲሰጡት ይጠይቃል፡፡
ባለጸጋው፤ “በል በቶሎ አሳውቀኝ” ብለውት ይሄዳሉ፡፡
(በልባቸው “ብትማከር ነው የሚሻልህ” ሳይሉት አይቀሩም!)
ፕሬዚዳንቱ፤ ወዲያው የኮሌጁን ቦርድ አስቸኳይ ስብሰባ ይጠራና በጉዳዩ ላይ ውይይት ይጀምራሉ፡፡ ብዙዎቹ አባላት የገንዘቡ መጠን የፈለገውን ያህል ብዙ ቢሆን፣ ለአህያ የክብር ዶክትሬት አንሰጥም ብለው ተፈጠሙ፡፡
አንድ በኮሌጁ ለረዥም ዓመታት ያገለገሉ ብልህ አዛውንት ግን ለፕሬዚዳንቱ የተለየ ሃሳብ አቀረቡ፡፡
“ገንዘቡን ተቀበልና ለአህያዋ የክብር ዶክትሬቱን ስጥ ባክህ; አሉት፡፡
ፕሬዚዳንቱም ደንገጥ ብሎ፤ “ይሄን ማድረግ ለኮሌጃችን ውርደት አይሆንም?” ሲል ጠየቃቸው፡፡
“በፍጹም አይሆንም; አሉ አዛውንቱ፤ “እንደውም ክብር ነው፤ ለምሉዕ አህያ የክብር ዶክትሬት ስንሰጥ በኮሌጁ ታሪክ የመጀመሪያችን ይሆናል!!”
(እስከዛሬ ድረስ ከአህያ ለማይሻሉ ሰዎች ስንሰጥ ከርመናል ማለታቸው ነው!!)

  • በክልሉ የተጀመረው እንቅስቃሴ ባለሃብቶችን ዋስትና የሚያሳጣና ሥጋት ላይ የሚጥል ነው
                • ቢዝነስ ከኢንቨስተሮች እየቀሙ ለወጣቶች መሸለሙ ዘላቂ መፍትሄ አይሆንም
                • ከባለሀብቶች የማዕድን ማውጫዎችን መንጠቅ የኮሚኒስቶች አካሄድ ነው

        የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ይፋ ያደረገው “የኢኮኖሚ አብዮት” እያነጋገረ ሲሆን ሰሞኑን ኦዳ ትራንስፖርት
ኩባንያን ለመመሥረት በግማሽ ቀን በተካሄደ የአክሲዮን ሽያጭ 617 ሚሊዮን ብር የሚያወጡ አክሲዮኖች መሸጣቸው ታውቋል፡፡ የኦዳ ትራንስፖርት አክሲዮን ማህበር በሙሉ አቅሙ ሲመሰረት ከወጣቶች ጋር በጋራ የሚያስተዳድራቸው የነዳጅ ማደያዎችና የነዳጅ ዲፖዎች እንደሚኖሩትም ተጠቁሟል፡፡ በሌላ በኩል የክልሉ መንግስት 1.2 ሚሊዮን ለሚደርሱ የኦሮሚያ ሥራ አጥ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር በሚል በባለሃብቶች ይዞታ ሥር የነበሩ የማዕድን
ማውጫ ቦታዎችን እየነጠቀ ለተደራጁ ወጣቶች ማከፋፈል የጀመረ ሲሆን ባለሃብቶች በዚህ እርምጃ መከፋታቸውን ገልፀዋል፡፡ ከ15 ዓመት በላይ በክልሉ በጠጠር ማዕድን ማውጣት ስራ ላይ ተሰማርተው ሲሰሩ እንደነበር የገለጹ አንድ ባለሀብት፤ “በዘርፉ የተሰማሩ አልሚዎችን አስወጥቶ ለኪሳራና ለውድቀት በመዳረግ ምንም ላልለፉ ወጣቶች ማከፋፈል በፍፁም ተቀባይነት የለውም” ሲሉ የክልሉን መንግስት እርምጃ ተቃውመዋል፡፡ ሌሎች የማዕድን ማውጫ ቦታቸውን የተነጠቁ ባለሀብቶችም “ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዜጋ የግል ሀብት የማፍራት መብት አለው” የሚለውን የህገ
መንግስቱን አንቀፅ 40 በመጥቀስ፣ህገ መንግስታዊ መብታቸው መጣሱን ጠቁመው አቤቱታቸውን ለመንግስት እያቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ በጉዳዩ ዙሪያ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችን፣ምሁራንና ጋዜጠኞችን አነጋግሮ አስተያየታቸውን እንደሚከተለው አጠናቅሮታል፡፡

                 “የሥራ ዕድል መፍጠር ያለበት መንግስት አይደለም”
                         ስዩም ተሾመ (ጦማሪና የዩኒቨርሲቲ መምህር

      ከባለሀብቶች የማዕድን ማውጫዎችን መንጠቅ የኮሚኒስቶች አካሄድ ነው፡፡ በስነ ምጣኔ አመክንዮ ስንመለከተው፤ መንግስት በተለያዩ ቢዝነሶች መግባቱም የሚደገፍ አይደለም፡፡ ከግለሰቦች የኢንቨስትመንት ቦታ መውረስም ሆነ መንግስት ነጋዴ መሆኑ በየትኛውም መንገድ አይደገፍም፡፡ ይሄ የኮሚኒስት ስርአት ባህሪ ነው፡፡ የክልሉ መንግስት ይሄን በማድረጉ ግለሰብ ባለሀብቶችን እየቀጣ ነው ማለት ነው፡፡
የስራ ዕድል መፍጠር ያለበት እኮ መንግስት አይደለም፡፡ የስራ ዕድል በገንዘብ አይገዛም። መፍጠር የሚችለው ማህበረሰቡ ራሱ ነው፡፡ መንግስት ኃላፊነቱ ምቹ ሁኔታ መፍጠር ነው፡፡ የፋይናንስ ስርአቱን፣ ቢሮክራሲውን ማስተካከል፣ የቢዝነስ ስልቶችን ማስተማር የመሳሰሉት ናቸው የመንግስት ኃላፊነቶች፡፡ ከባለሀብቶች ላይ ሀብት ቀምቶ ለስራ አጥ ወጣቶች ማከፋፈል ፈፅሞ ተቀባይነት የሌለው ነው፡፡ ይሄ ማለት እናለማለን ያሉትን ኢንቨስተሮች እንደ መቅጣት ነው፡፡ እነዚህ ተነጥቆ የሚሰጣቸው ወጣቶችም ቢሆኑ በሙሉ ፍላጎታቸው ሳይሆን በመንግስት ግፊትና ድጎማ ወደ ስራው ስለሚገቡ ውጤታማ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ በግላቸው ተሯሩጠው አዲስ የስራ መስክ የፈጠሩትን ሰዎች እየቀጡ፣ የቢዝነስ ክህሎት ለሌላቸው ስራ አጦች መሸለም በየትኛውም አካሄድ አይደገፍም፡፡ ቢዝነስ ከግለሰቦች እየቀሙ ለስራ አጥ መሸለሙ ወጣቶችን ምርታማ አያደርግም። ምክንያቱም እነሱ ስለ ቢዝነሱ በቂ እውቀት አይኖራቸውም፡፡ ለወጣቶች የስራ ዕድል መፍጠር የሚቻለው በዚህ መርህና አካሄድ አይደለም፡፡ ተወዳዳሪና ብቁ የቢዝነስ ሰዎችንም በዚህ አካሄድ መፍጠር አይቻልም፡፡ የአለም ተሞክሮም ይሄን አያሳይም፡፡ ሰዎች በሚሰሩት ስራ በቂ እውቀት፣ ፍላጎትና ክህሎት ሲኖራቸው ነው ውጤታማ ሊሆኑ የሚችሉት፡፡
በሌላ በኩል መንግስት ከባለሀብቱ ልጣመርና ቢዝነስ ላቋቁም የሚለውም የሚያስኬድ አይደለም፡፡ ከዚህ በፊትም ታይቶ ውጤት ያላመጣ አካሄድ ነው። በነዚህ አካሄዶች ቀደም ሲል ህዝቡ ሲጠይቃቸው ለነበሩ ጥያቄዎች መልስ ማግኘት አይቻልም፡፡ ተወዳዳሪ የቢዝነስ ሰዎችን ለመፍጠር በመጀመሪያ የሚደራጁት ሰዎች ብቃትና ፍላጎት ወሳኝነት አለው፡፡ ዝም ብሎ አደራጅቶ ሀብት ውረሱ ማለት እንዴት ውጤት ያመጣል? እነዚህ ሰዎች በምንም መመዘኛ ተወዳዳሪ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ እየጨመረ ለሚሄደው የስራ ዕድል ፍላጎትም ተጨማሪ የስራ ዕድል አይፈጥርም፡፡
በሌላ በኩል በኦሮሚያ በነበረው ተቃውሞ ወደ አደባባይ የወጡት ወጣቶች ጥያቄ በእርግጥስ የስራ ማጣት ጥያቄ ብቻ ነው? የሚለውንም መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ እንደ‘ኔ የነበረው ጥያቄ የእኩልነትና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ጥያቄ ነው፡፡ ይሄን ደግሞ ከአንዱ ነጥቆ ለሌላው በመስጠት ማስታገስ አይቻልም፡፡ በአመፁ ወቅት በዋናነት የተነሳው ጥያቄ፤ ከፊንፊኔ ዙሪያ የሚፈናቀሉ ሰዎች መብትና ጥቅማቸው አልተከበረላቸውም የሚል ነው፡፡ ይሄን ደግሞ በዚህ መንገድ ለመፍታት መንቀሳቀስ ከስነ ምጣኔ መርህ አንፃር አያስኬድም፡፡ የመብት ጥያቄዎች ባልተመለሱበት ሁኔታ ይሄን ቁንፅል እርምጃ ለመውሰድ መሞከር ትክክል አይደለም፤ ውጤትም አያመጣም፡፡   

-------------------

                          “ባለሃብቶች የሚወረሱ ከሆነ ምን ዋስትና ይኖራቸዋል?”
                         አቶ ጥሩነህ ገሞታ (የኦፌኮ አመራር)

        የኢኮኖሚና የፖለቲካ ሪፎርም ማድረግ የሚደገፍ ጉዳይ ነው፡፡ ይሄን ማንም አይቃወምም፡፡ ዋናው ሪፎርሙ የሚፈለገውን ለውጥ ማምጣት ይችላል ወይ የሚለው ነው፡፡ አሁንም አድሮ ቃሪያ አይነት ከሆነ ግን ምንም ውጤት ስለሌለው አይደገፍም። በኦሮሚያ ክልል በመንግስት በሚገለፀው ደረጃ የሪፎርም ስራ ሲሰራ አላየንም፡፡ የሚታይ ነገር ካለ ግን የምንቀበለው ይሆናል፡፡
ለወጣቶች በሚል ከባለሀብቶች የሚነጠቁ ፕሮጀክቶችን በተመለከተ አንድ ምሳሌ ማንሳት ይቻላል፡፡ በ1967 ደርግ የገጠር መሬትና የከተማ ቤትና ቦታ እንዲሁም ፋብሪካዎችንና ኢንዱስትሪዎችን ወረስኩ ሲል የነበረውን ያስታውሳል፡፡ ደርግ በወቅቱ የግለሰቦችን ወፍጮ ቤቶች ሳይቀር ወርሷል፡፡ የተቧደኑ ግለሰቦች ማህበር በሚል እየተቋቋሙ ወፍጮ ቤትና የተለያዩ የሰው ንብረቶችን የወሰዱበት ጊዜ ነበር፡፡ ይሄም አካሄድ ያንን የሚያስታውስ ነው፡፡ አሁንም ቢሆን ስርአቱ የግል ባለሃብቶች ኢንቨስት አድርገው ሀብት ማፍራት ይችላሉ የሚል ፖሊሲ በማስቀመጡ ነው ግለሰቦች ዋስትና አለን ብለው ተማምነው ኢንቨስት የሚያደርጉት፡፡ እነዚህ ግለሰቦች በህግ አግባብ ግዴታቸውን እየተወጡ ያሉ ከሆነና ይህን ችላ ብሎ ልማታቸውን የሚነጥቅ ከሆነ የሚደገፍ አይደለም፡፡ ቀድሞውኑ በህገ ወጥ ሁኔታ የያዙት ከተወረሱ ግን እንደተወረሱ አይቆጠርም፡፡ ህጋዊዎች በዚህ መንገድ ዋስትና አጥተው የሚወረሱ ከሆነ ግን ለወደፊት ኢንቨስተሮች ምን ዋስትና ይኖራቸዋል? የሀገራችንን የሰው ኃይል ቀጥረው ሊያሰሩና ስራውን ሊያሳድጉ የሚችሉ ኢንቨስተሮች ከየት ሊመጡ ይችላሉ? የሚል አስደንጋጭ ጥያቄም ያስነሳል፡፡ ስለዚህ ባለሀብቶች በዚህ መልኩ ሀብታቸውን እየተነጠቁ ከሆነ በግልም ሆነ በፓርቲያችን ደረጃ አንቀበለውም፡፡
ወጣቶችን ወደ ስራ ማስገባት ከተፈለገ‘ኮ ካፒታል መድቦ አዳዲስ የቢዝነስ እቅዶችን አውጥቶ ማሰማራት ይቻላል፡፡ ይሄ ከተደረገ ብቻ ነው የምንደግፈው፡፡ የሰው ሀብት ነጥቆ ለሌላ መስጠት ግን የማይደገፍ ነው፡፡ ወጣቶችን በፓርቲ ደረጃ ጠርንፎ ከመያዝ ወጣቱን ለቀቅ አድርጎ፣ በፈለገበት የስራ መስክ እንዲሰማራ ማድረግ ነው የሚያስፈልገው፡፡ የወጣቶችን አቅም አጎልብቶ ወደ ስራ እንዲገቡ ከማድረግ ይልቅ የሌሎችን ሀብት ወርሶ መስጠት ተገቢ አይደለም፡፡ አላስፈላጊ ከሆኑ በጀቶች እየቀነሱ የተለያዩ ዘርፎች ላይ ማሰማራት ይቻል ነበር፡፡ ይሄ የሚደረገው ለህዝባዊ እንቅስቃሴው ምላሽ ለመስጠት ከሆነ፣ ህዝቡ ያነሳው የኢኮኖሚ ብቻ ሳይሆን የመብት ጥያቄም ነው፡፡ በዚህ ብቻ ለማስተንፈስ ከተፈለገ ዘላቂ ውጤት ያመጣል የሚል እምነት የለኝም፡፡

----------------------

                       “ከአንዱ ነጥቆ ለአንዱ መስጠት አይበረታታም”
                          አቶ ቶሎሣ ተስፋዬ (የኦሮሞ ብሄራዊ ኮንግረስ ሊቀመንበር)

       እኛ በህዝቡ የሚሰሩትን የልማት ስራዎችና ህዝቡ የሚቀበላቸውን ነገሮች ሁሉ እንደግፋለን። ወጣቱ የስራ እድል ጥያቄ እንዳለው ይታወቃል፡፡ ለዚህ የወጣቶች ጥያቄ እንደ ሀገርም እንደ ኦሮሚያ ክልልም እየተቀመጡ ያሉ የመፍትሄ አቅጣጫዎችን በበጎ እንቀበላቸዋለን፡፡ በተለይ የኦሮሚያ “የኢኮኖሚ አብዮት” ብዙ ወጣቶችን ያሳትፋል የሚል እምነት አለን፡፡ መንግስት ቆም ብሎ አስቧል፤ ችግሩን አይቷል፤ የህብረተሰቡን ክፍል በየደረጃው አወያይቷል፡፡ በዚህም ችግሩን ለይቶ አውቋል የሚል ግምት አለን፡፡ ችግሩን ለይቶ ካወቀ በኋላ እየወሰደ ያለው የመፍትሄ እርምጃ የሚበረታታ ነው፡፡ ህዝብም ድጋፍ እየቸረው ነው፡፡ ሰሞኑን በተደረገው የአክሲዮን ሽያጭ ላይ ከፍተኛ ገንዘብ መገኘቱ፣ ህዝቡ ለዚህ ድጋፍ እንዳለው ያመላክታል፡፡
ከዚህ ቀደም እንደ ፓርቲ ስንለው የቆየነውን ነው አሁን መንግስት እየሰራ ያለው፡፡ በተደጋጋሚ ወጣቱ ስራ አጥ ሆኗል፤ ጥቂቶች ሀብት ያለአግባብ እያካበቱ ነው ስንል ነበር፡፡ በተለይ ከአመራሩ ጋር ቅርበት ያላቸው ጥቂት ሰዎች፣ በኦሮሚያ ውስጥ ከፍተኛ ሀብት እያካበቱ የሀብት ክፍፍሉ ከፍተኛ ልዩነት እያሳየ ነው፡፡ አብዛኛው የሚበላው እያጣ ነው፡፡ በተለይ ወጣቱና የተማረው ክፍል ተረስቷል እያልን ስንጮህ ቆይተናል፡፡ ለዚህ ጩኸት ምላሽ እየተሰጠ ይመስላል፤ የተጀመረው ነገር ጥሩ ነው፣ ውጤት ያመጣል የሚል እምነትም አለን፡፡
ይህን ስንል ግን ከአንዱ ነጥቆ ለአንዱ መስጠትን አናበረታታም፡፡ መጀመሪያውኑ ከባለሀብቶች ጋር በኦሮሚያ ውስጥ ሲሰራ የቆየው ፍትሃዊነት የሌለው ነበር፡፡ አንድ ባለሀብት የህዝብ መሬት ይዞ አጥሮ፣ አስርና ከዚያ በላይ ዓመት ያለምንም ጥቅም ማቆየትና መሬቱን አትርፎ ለመሸጥ ገበያ የመጠባበቅ አዝማሚያ ነበር፡፡ በእነዚህ ዓይነቶቹ ላይ እርምጃ መወሰዱ የሚበረታታ ነው፡፡ ነገር ግን በህጋዊ መንገድ ከሚሰራው ላይ የሚነጠቅ ከሆነ ተቀባይነት የለውም፡፡ ብዙ የተማሩና ልምዱ ያላቸው ወጣቶች አሉ፤ እነዚህ ወጣቶች መነሻ ካፒታል ማግኘታቸው ስራቸውን ውጤታማ ለማድረግ ያስችላቸዋል፡፡
በህጋዊ መንገድ እየሰራ፣ ሀገርን እየጠቀመ ያለን ኢንቨስተር መሬትና ሀብት እየነጠቁ ለወጣቱ እንሰጣለን የሚባለውን እኛ አንቀበለውም፡፡ ሁሉም እኩል ተጠቃሚ የሚሆንበትና በቀጣይ ጥያቄ የማይነሳበት አሰራር ነው መፈጠር ያለበት። ባለሀብቶችን ከስራ ውጪ አድርጎ ለሌላ ወገን መስጠት በየትኛውም መመዘኛ የሚበረታታ አይደለም፡፡ ሁሉም ዜጎች ፍትሃዊ ተጠቃሚ መሆን አለባቸው፡፡

------------------

                          “የኢኮኖሚ አብዮት እንደቃሉ ቀላል አይሆንም”
                             በፍቃዱ ኃይሉ (ጦማሪና ጋዜጠኛ)

          ኢህአዴግ የሚከተለው የፖለቲካል ኢኮኖሚ ስትራቴጂ በየወቅቱ የሚቀያየር በመሆኑ በግልፅ አይገባኝም፡፡ በአሁን ወቅት በዓለም ላይ ያለውን ሰፊ ሁኔታ ስንመለከት፣ ወደ ነፃ ኢኮኖሚ ያዘመመ በመሆኑ፣ ይህን ብንከተል የተሻለ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ ከዚህ አንፃር ባለሀብቶች በህጋዊ መንገድ ያገኙትን የኢንቨስትመንት እድል ለወጣቶች ስራ ፈጠራ በሚል መንጠቅ ወንጀልም ጭምር ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ኢንቨስተሮችን ዋስትና አሳጥቶ ኢንቨስት ከማድረግ እንዲቆጠቡ ያደርጋል። ይሄ አካሄድ ወጣቶች ኢንቨስትመንቶችን አቃጠሉ ከተባለውም የባሰ ነው፡፡ ኢንቨስተሮች ይሄንን እያዩ ከዚህ በኋላ እንዴት ኢንቨስት ሊያደርጉ ይችላሉ? ከዚህ አንፃር አካሄዱ ፈፅሞ ትክክል አይደለም፡፡ በጣም አስደንጋጭና አሳዛኝ ነው የሚሆነው፡፡
በእርግጥ ለወጣቶች የስራ ዕድል መፈጠር አለበት፤ ነገር ግን አዳዲስ እድል መፍጠር እንጂ የሌላውን መሻማት አግባብ አይሆንም፡፡ ለምሳሌ የማዕድን ማውጫዎችን በተመለከተ ወጣቶቹ ከባለሀብቶቹ ጋር በሰንሰለታማ የንግድ ስርአት ተቀናጅተው እንዴት መስራት እንደሚችሉ የፖሊሲ አቅጣጫዎችን ማስቀመጥ እንጂ ንብረት እየነጠቁ መስጠት አያዋጣም፡፡ ነገ ከነገ ወዲያም ሌላ መዘዝ ይዞ ነው የሚመጣው፡፡
በተለይ ስለ ማክሮ ኢኮኖሚ ዘላቂነት ስናስብ፣በዚህ አካሄድ ኢንቨስተሮችን እያቀጨጩ እንዴት መጓዝ ይቻላል? የሚለው አጠያያቂ ነው፡፡
የኦሮሚያ ክልል ያመጣው “የኢኮኖሚ አብዮት” ቃሉ በጣም ማራኪ ነው፡፡ የኢኮኖሚ አብዮት በእርግጥም ያስፈልገናል፡፡ ግን እንደ ቃሉ ቀላል አይሆንም፡፡ እርግጥ ነው ማህበረሰቡ ከአካባቢው ከሚገኘው ሀብት ተጠቃሚ ሊሆን ይገባዋል፡፡ ነገር ግን ኢንቨስተሮች በሚሰሩት ልማት ወጣቶች ተቀጥረው በመስራት ተጠቃሚ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ እነዚህን ጥቅሞች ለየአካባቢው ወጣቶች ማስጠበቅ ነው የሚሻለው፡፡  

• የግል ቤት የሌላቸው የክልሉ ተወላጆችና የኦሮሚያ ዳያስፖራዎች ተጠቃሚ ይሆናሉ
• የመጠጥ አምራች ኩባንያና የሲሚንቶ ፋብሪካ አክሲዮኖች ለክልሉ ተወላጆች ይቀርባሉ

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት፣ ተወላጆቹ በሙሉ በክልሉ ከተሞች የመኖሪያ ቤት መስሪያ የከተማ ቦታ በነፃ እንዲያገኙ ወሰነ፡፡
በክልሉ የሚገኙ አርሶ አደሮች፣ አርብቶ አደሮች፣ የግል መኖሪያ ቤት የሌላቸው የከተማ ነዋሪዎች፣ ወጣቶች፣ መምህራንና የመንግስት ሰራተኞችን ጨምሮ የኦሮሚያ ዳያስፖራዎች በሙሉ የመኖሪያ ቤት መስሪያ የከተማ ቦታ በነፃ እንዲያገኙ መወሰኑን የኦሮሚያ የከተማ ቤቶች ልማት ም/ሃላፊ አቶ ሽመልስ አብዲሣ ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል፡፡
የክልሉ መንግስት ከዚህ ውሣኔ ላይ የደረሰው የክልሉ ከተሞች የተወላጆችን ጥቅም ባማከለ መልኩ እንዲያድጉና ተወላጆች በከተሞች ድርሻ እንዲኖራቸው ለማድረግ መሆኑም ተገልጿል፡፡ የክልሉ መንግስት ባደረገው ግምገማ፤ የቤት ኪራይ ዋጋ ውድነት ነዋሪዎችን ላልተፈለገ ወጪ መዳረጉንና እንዳይረጋጉ ማድረጉን፣ ቀደም ሲል በነበረው አካሄድ የክልሉ ከተሞች እድገትም በሚፈለገው መጠን አለመሆኑን እንዲሁም የክልሉን መሬት ለህገ ወጥ ደላሎች ያጋለጠ አሰራር እንደነበረ ደርሶበታል፡፡ እነዚህን ችግሮች ከግምት ውስጥ በማስገባትም ዜጎች የቤት መስሪያ የከተማ ቦታ እንዲያገኙ የሚያስችለው ደንብና መመሪያ ሊወጣ መቻሉን ም/ሃላፊው ጠቁመዋል፡፡
‹‹ህብረተሰቡ የከተማ ህይወት እንዲኖር ይፈለጋል›› ያሉት አቶ ሽመልስ፤ ይህ የክልሉ መንግስት እቅድ ይሄን ለማሳካት ያለመ በመሆኑ አርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ በዚህ ማዕቀፍ እንዲካተቱ መደረጉን አብራርተዋል፡፡ ከመከላከያ ሰራዊት ጡረታ የወጡ ግለሰቦችና ሌሎች የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችም የዚህ ፕሮጀክት ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ታውቋል፡፡  
በአካባቢው ለሁለትና ከዚያ በላይ ዓመት የኖሩ፣ የቤት መስሪያ ገንዘብ መቆጠብ የሚችሉና ቀሪ ገንዘብ መንግስት በሚያመቻቸው ብድር ለማግኘት ፍቃደኛ የሆኑ ግለሰቦች የቤት መስሪያ ቦታ ለማግኘት መደራጀት እንደሚችሉ ሃላፊው አስረድተዋል፡፡
ቦታ ፈላጊዎች የሚደራጁት በ4 አይነት አማራጮች ነው ተብሏል፡፡ በጋራ አፓርትመንት ለመገንባት የሚፈልጉ፣ G+1 እና ከዚያ በላይ መገንባት የሚፈልጉ እንዲሁም ቪላ ቤት መስራት የሚችሉ በሚል ሲሆን ይሄን ለማድረግ አቅም የሌላቸው መለስተኛ ቤቶችን ለመስራት የሚችሉባቸው አማራጮች መቀመጣቸውን አቶ ሽመልስ አብራርተዋል፡፡
የክልሉ መንግስት በዝቅተኛ ወጪ ቴክኖሎጂ ተጠቅመው የሚገነቡ የቤት አማራጮችን እያጠና መሆኑም ተገልጿል፡፡ አንድ ግለሰብ ለመኖሪያ ቤት መስሪያ የተሰጠውን ቦታ መሸጥ መለወጥና ከህጋዊ ወራሾች በስተቀር ለ3ኛ ወገን ማስተላለፍ እንዲሁም በውክልና ማሰራት አይችልም ብለዋል፤ ሃላፊው፡፡ እስከ 10 ዓመት ድረስም ካርታ እንደማይሰጥ አክለው ገልፀዋል፡፡ በነዚህ ጥብቅ መመሪያዎች እንዲታጠር የተደረገው የመሬት ብክነትንና ያለአግባብ መገልገልን ለማስቀረት በማሰብ ነው ተብሏል፡፡  
በክልሉ ከ9 ዓመት በላይ መሬት በዚህ መልክ ተሰጥቶ እንደማያውቅ የጠቆሙት አቶ ሽመልስ፤ የክልሉ መንግስት ይሄን ሰፊ እቅድ ሲተገብር ሊያጋጥሙ የሚችሉ ተግዳሮቶችንም በዝርዝር መለየቱን አስታውቀዋል፡፡ ከተለዩ ተግዳሮቶች መካከል የመሬት አቅርቦት አንዱ መሆኑን የጠቀሱት ሃላፊው፤ በተለይ ለአርሶ አደሮች የሚከፈል የመሬት ካሳና መንግስት መሬቱን ያለምንም የሊዝ ክፍያ ገቢ ሳያገኝበት በነፃ ለፈላጊዎች ማስተላለፉ ጫና ሊፈጥርበት እንደሚችል ጠቁመው፣ ለዚህም የተለያዩ አማራጮች እየተፈተሹ መሆኑን አስረድተዋል። ሌላው ተግዳሮት ለብድር አቅርቦት የሚሆን የፋይናንስ አቅም ሲሆን ይህንንም የቁጠባ ባህልን በማሳደግ ለመፍታት ጥረት ይደረጋል ብለዋል፡፡
የክልሉ መንግስት ለዚህ ፕሮጀክት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ ሰፊ ዝግጅት ማድረጉ የተገለጸ ሲሆን በአሁን ወቅትም ቤት የሌላቸውን ሰዎች ለይቶ የማደራጀት ስራ እየተሰራ ነው ተብሏል፡፡ የመሬት አቅርቦቱም ሰዎች በፈለጉት የቤት አይነት ተደራጅተው ሲቀርቡ ወዲያው የሚፈፀም መሆኑ ተገልጿል፡፡
በሌላ በኩል የክልሉ መንግስት ይፋ ባደረገው ‹‹የኢኮኖሚ አብዮት››፣ ከኦዳ ትራንስፖርት አክሲዮን በተጨማሪ በቅርቡ የተለያዩ መጠጥ አምራች ኩባንያና የሲሚንቶ ፋብሪካ አክሲዮኖችን ለክልሉ ተወላጆች በሽያጭ ለማቅረብ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ የመንገድ ትራንስፖርት ሃላፊ አቶ ታከለ ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡

የድርድሩ ቀጣይ እጣ ፈንታ በኢህአዴግ እጅ ነው”

ከገዥው ፓርቲ ጋር የቅድመ ድርድር መመሪያ ላይ ውይይት እያደረጉ ያሉት 20 ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ ያለ ገለልተኛ አካል ድርድር እንደማይኖር ያስታወቁ ሲሆን ኢህአዴግ ጉዳዩን ለማጤን ቀጠሮ ወስዷል፡፡
ፓርቲዎቹ ባለፈው ቅዳሜ መጋቢት 9፣ ቀኑን ሙሉ ባደረጉት ውይይት ቀደም ሲል በዙር መድረክ እየመራን እንደራደር የሚል ሃሳብ ያቀረቡ ተቃዋሚዎች አቋማቸውን ለውጠው፣ ድርድር ያለ ገለልተኛ አደራዳሪ አይሆንም ሲሉ የተፈጠሙ ሲሆን ኢህአዴግና አንድ ተቃዋሚ ፓርቲ በዙር መድረክ እየመራን መደራደር አለብን በሚል አቋም በመጽናታቸው መግባባት ላይ ሳይደረስ ቀርቷል። ይሄን ተከትሎም ኢህአዴግ ጉዳዩን በድጋሚ ለማጤን ጊዜ እንዲሰጠው የጠየቀ ሲሆን በመጪው ረቡዕ መጋቢት 20፣ አቋሙን እንደሚያሳውቅ ይጠበቃል፡፡
የቅዳሜውን ውይይት አስመልክቶ ያነጋገርናቸው የመኢአድ ም/ፕሬዚዳንት አቶ ሙሉጌታ አበበ፤ በእለቱ ሁሉም ተቃዋሚዎች ገለልተኛ አካል ያደራድረን የሚል አቋም መያዛቸው ያልጠበቁት መሆኑን ገልፀው፤ “ፓርቲያችን በአደራዳሪዎች ገለልተኛነት ላይ የተሸራረፈ አቋም የለውም›› ብለዋል፡፡ ኢህአዴግ አቋሙን ካልቀየረ የድርድሩ ቀጣይነት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እንደሚኖረውም አቶ ሙሉጌታ አስታውቀዋል፡፡
የኢዴፓ ዋና ፀሃፊ አቶ ዋሲሁን ተስፋዬ በበኩላቸው፤ ከአንድ ተቃዋሚ ፓርቲ በስተቀር ሌሎቹ ገለልተኛ አካል ያደራድረን የሚለው አቋማቸው የፀና መሆኑን ጠቁመው፤ ኤዴፓም ይሄን አቋም እንደማይቀይር ተናግረዋል፡፡ ‹‹ገለልተኛ አካል ካላደራደረ ኢዴፓ በድርድሩ ሊቀጥል አይችልም›› ብለዋል - አቶ ዋሲሁን፡፡
“ኢህአዴግ ወደ ብዙኃኑ አቋም ይመጣል የሚል ተስፋ አለኝ” ያሉት የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ የሸዋስ አሰፋ፤ የድርድሩ ቀጣይ እጣ ፈንታ በኢህአዴግ እጅ ነው ብለዋል፡፡  
21 ፓርቲዎች የሚያደርጉት ስብሰባ ውይይት እንጂ ድርድር ሊባል አይችልም የሚል አቋሙን ያፀናው መድረክ በበኩሉ፤ በዚህ ሁኔታ በድርድሩ እንደማይቀጥል የአመራር አባሉ አቶ ጥላሁን እንደሻው ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል። መድረክ ለገዥው ፓርቲ ሁለት አማራጮችን ማቅረቡን የጠቆሙት አቶ ጥላሁን፤አንደኛው ተቃዋሚዎች በመድረክ እንዲወከሉና ከኢህአዴግ ጋር እንዲደራደሩ አሊያም ኢህአዴግ ከሌሎቹ ጋር ከሚያደርገው ድርድር ጎን ለጎን ለብቻው ከመድረክ ጋር እንዲደራደር ሀሳብ አቅርቦ ምላሹን በመጠባበቅ ላይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ኢህአዴግ ለዚህ ፍቃደኛ ካልሆነ መድረክ ከ21 ፓርቲዎች ጋር  ለድርድር እንደማይቀርብና ከድርድሩ እንደሚወጣ አቶ ጥላሁን አስታውቀዋል፡፡
‹‹ምንም ውጤት ያላመጣውን የፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤትን የሚመስል ውይይት እንዲደረግ አንፈልግም” ያሉት የአመራር አባሉ፤ ‹‹የህዝቡን ችግር ነቅሰን አውጥተን ተጨባጭ መፍትሄ እንዲሰጥባቸው ነው የምንፈልገው” ብለዋል፡፡ ‹‹የታሰሩ ፖለቲከኞችም እንዲፈቱ ከተፈለገ ጠንካራ ድርድር ማድረግ አለብን›› ሲሉም አክለዋል፡፡   

የደብሩ አስተዳደር ይግባኝ ጠይቋል

       በአዲስ አበባ የካ ክፍለ ከተማ፣ ወረዳ 12 ውስጥ የምትገኘው፣ የየካ አባዶ ደብረ ልዕልና ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን፣ በሕገ ወጥ ይዞታ ላይ፣ ያለግንባታ ፈቃድ መሠራቷን የገለጸው ፍ/ቤት፣ እንድትፈርስ ወሰነ፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት፣ የካ ምድብ ችሎት፣ ባለፈው ረቡዕ በሰጠው ውሳኔ፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ እንዳትፈርስ በደብሩ ለቀረበው የ“ሁከት ይወገድልኝ” ክሥ፣ ኅዳር 28 ቀን 2009 ዓ.ም አስተላልፎት የነበረውን የእግድ ትእዛዝ ማንሣቱን አስታውቋል፡፡
በከሣሽ የደብረ ልዕልና ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያንና በተከሣሽ የወረዳው ደንብ ማስከበር ጽ/ቤት መካከል የቀረቡትን አቤቱታዎችና ሲካሔድ የቆየውን የቃል ክርክር መመርመሩን የገለጸው ፍ/ቤቱ፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ የተሠራችበትን ቤትና ቦታ፣ ከሰኔ 24 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ በስጦታ ያስተላለፉት ግለሰቦች፤ ይዞታውን በሕጋዊ አግባብ እንዳገኙት የሚያስረዳ ማስረጃ በከሣሽ በኩል አለመቅረቡን ጠቅሷል፡፡
ቤቱም፣ የሚመለከተው የከተማው አስተዳደር የግንባታ ፈቃድና ቁጥጥር ጽ/ቤት ፈቃድ ሰጥቶ ስለመሠራቱ ማስረጃ አለመቅረቡንና በመሥመር ካርታ ወይም በ1997 ዓ.ም የአየር ካርታ ላይ እንደማይታይ፣ የክፍለ ከተማው የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ጽ/ቤት ማረጋገጡን አስረድቷል፡፡
ለክሡ መነሻ የሆነው ቤት፣ የቤተ ክርስቲያን ቅርጽ እንዲኖረው ተደርጎ የተሠራውም፣ በሕግ ሥልጣን ከተሰጠው የከተማው አስተዳደር አካል፣ የግንባታ ፈቃድ ሳይገኝ መሆኑን በውሳኔው ጠቅሷል፡፡
የወረዳው ደንብ ማስከበር ጽ/ቤት፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ እንድትፈርስ፣ ለደብሩ የሰጠው ማስጠንቀቂያ፣ በሕግ የተሰጠውን ሓላፊነት መወጣቱ እንጂ የሁከት ተግባር አይደለም፤ በደብሩ የቀረበውም ክሥ ተቀባይነት የለውም፤” ሲል ወስኗል፡፡ ለክሡ መነሻ በሆነው ግንባታ ላይ ቀደም ሲል ተላልፎ የነበረው የእግድ ትእዛዝ መነሣቱንም አስታውቋል፡፡  
በሌላ በኩል፣ የደብረ ልዕልና ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር፣ የፍ/ቤቱን ውሳኔ በመቃወም ይግባኝ መጠየቁ ታውቋል፡፡  

  ሁለት ዳኞች አዲሱን የትራምፕ የጉዞ ገደብ አግደውታል

     ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ አሜሪካ በተባበሩት መንግስታት ድርጅትና በራሱ ለጋሽ ድርጅቶች በኩል ለአለማቀፍ እርዳታና ለልማት የምትሰጠውን የገንዘብ መጠን በ28 በመቶ ያህል ለመቀነስ የሚያስችል ምክረ ሃሳብ ማቅረባቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ምክረ ሃሳቡ በኮንግረስ ተቀባይነት ካገኘ ኢትዮጵያን ጨምሮ ለበርካታ የአለማችን አገራት የልማት እርዳታ የሚያደርገው የዩኤስ አይዲ አመታዊ ድጋፍ በ28 በመቶ ያህል ይቀንሳል ያለው ዘገባው፤ በሌሎች ተቋማትና መስኮች የተያዙ በጀቶችም በከፍተኛ ሁኔታ ቀንሰው ብዙዎችን ተጎጂ እንደሚያደርጉ ገልጧል፡፡
አነጋጋሪ የሆነው የትራምፕ የበጀት ቅነሳ ምክረ ሃሳብ፣ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም በጀት በ31.4 በመቶ፣ የጤናና የሰብአዊ አገልግሎቶች በጀት በ16.2 በመቶ፣ የግብርና ዘርፍ በ21 በመቶ፣ የትራንስፖርት ዘርፍ በ13 በመቶ ቅነሳ እንዲደረግባቸው የሚጠይቅ መሆኑንም አስረድቷል፡፡
የትራምፕ የበጀት ቅነሳ ምክረ ሃሳብ ከፍተኛ ተቃውሞ ይገጥመዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ዘገባው፤ ምክረ ሃሳቡ መከላከያን ጨምሮ በአንዳንድ ዘርፎች ከፍተኛ የበጀት ጭማሪ እንደሚያደርግ ገልጾ፣ ሃሳቡ ተቀባይነት ካገኘ የመከላከያ ወጪ በ10 በመቶ ወይም በ54 ቢሊዮን ዶላር እንደሚያድግ አብራርቷል፡፡
በተያያዘ ዜናም የሃዋይ እና የሜሪላንድ የፌዴራል ፍርድ ቤት ዳኞች ተሻሽሎ የወጣው የትራምፕ የጉዞ ገደብ ተፈጻሚ እንዳይሆን ማገዳቸው ተነግሯል። ዳኞቹ የስድስት አገራት ዜጎች ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ የሚከለክለውን አዲሱ የጉዞ ገደብ ትዕዛዝ ህጋዊነትም ሆነ አግባብነቱን የሚያረጋግጥ በቂ ማስረጃ የለውም በሚል እንዳይተገበር የሚያግድ ትዕዛዝ ማውጣታቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡

 ራፐሩ ስኑፕ ዶግ ትራምፕን ተኩሶ ሲገድላቸው የሚያሳይ ቪዲዮ ለቋል

      የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ የታንዛኒያውን አቻቸውን ጆን ማጉፋሊን በማድነቅ ሌሎች የአፍሪካ መሪዎችን አጣጣሉ የሚል ሃሰተኛ መረጃ ያሰራጩ ቲቢሲ የተሰኘው የታንዛኒያ የብሮድካስቲንግ ተቋም ባልደረቦች የሆኑ 9 ጋዜጠኞች ከስራ መታገዳቸው ተዘግቧል፡፡
ጋዜጠኞቹ “ትራምፕ ሙጉፋሊን የአፍሪካ ጀግና ሲሉ የአመራር ብቃታቸውን በማድነቅ አሞካሽተዋቸዋል፣ ሌሎች የአፍሪካ መሪዎች ግን አንዳች እንኳን ፋይዳ ያለው ነገር እየሰሩ አይደለም ሲሉ ተናግረዋል” የሚለውን ሃሰተኛ መረጃ በማሰራጨታቸው ከስራ መታገዳቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ትራምፕ የተቀሩት የአፍሪካ መሪዎች ከታንዛኒያው ፕሬዚዳንት ሙጉፋሊ ሊማሩ ይገባል ብለዋል በማለት ሃሰተኛ መረጃ ያሰራጩት ጋዜጠኞቹ፤ ከሙጉፋሊ ብቃቶች መካከል ሙስናን በመዋጋት ረገድ ያሳዩት ቁርጠኝነት አንዱ ነው ማለታቸውንም አትተዋል፡፡
በተያያዘ ዜና ደግሞ ታዋቂው ራፐር ስኑፕ ዶግ፤ ዶናልድ ትራምፕን ተኩሶ ሲገድላቸው የሚያሳይ የሙዚቃ ቪዲዮ ሰሞኑን መልቀቁን ተከትሎ፣ ፕሬዚዳንቱ “ስኑፕ ዶግ በዚህ አጉል ድርጊቱ ሳቢያ ሊታሰር ይገባል” ማለታቸው ተዘግቧል፡፡
ትራምፕ በትዊተር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ስኑፕ ዶግ በቪዲዮው ሲገድል ያሳየው ኦባማን ቢሆን ኖሮ ወደ እስር ቤት ነበር የሚገባው ማለታቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ የትራምፕ የግል ጠበቃ ማይክል ኮሄን በበኩላቸው ቪዲዮውን ሲመለከቱ በእጅጉ መደንገጣቸውን በማስታወስ፣ ስኑፕ ዶግ ፕሬዚዳንቱን አዋርዷል ይቅርታ ሊጠይቃቸው ይገባል ማለታቸውን ገልጧል፡፡

  - ከ43 አመታት በፊት በፈጸመው ግድያ ተከስሶ ፍ/ ቤት ቀርቧል
                    - የእድሜ ልክ እስራት ተፈርዶበት ያለፉትን 23 አመታት በእስር አሳልፏል

      ካርሎስ ቀበሮው በሚል ስሙ የሚታወቀውና ከአለማችን ቀንደኛ ገዳዮች አንዱ እንደሆነ የሚነገርለት ኢሊች ራሚሬዝ ሳንቼዝ፣ እስር ቤት ከመግባቱ በፊት ብዙ ሰዎችን ባለመግደሉ እንደሚጸጸት፣ ከ43 አመታት በፊት በፓሪስ በሚገኝ የገበያ ማዕከል በተፈጸመ ወንጀል ተከስሶ ባለፈው ሰኞ ፍርድ ቤት በቀረበበት ወቅት መናገሩ ተዘገበ፡፡
እ.ኤ.አ በ1974 የተከሰተውንና 2 ሰዎች ለሞት፣ 34 ሰዎች ደግሞ ለመቁሰል አደጋ የተዳረጉበትን የቦምብ ጥቃት ፈጽሟል በሚል ፍርድ ቤት የቀረበው ካርሎስ፤ ከመታሰርህ በፊት በነበረህ የገዳይነት ህይወት ዘመንህ የምትጸጸትበት ነገር አለ? በሚል ከዳኛው የቀረበለትን ጥያቄ ሲመልስ፣ “አዎ… ልገድላቸው ሲገባኝ ያልገደልኳቸውን ሰዎች ሳስብ ይጸጽተኛል” ማለቱን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
የ67 አመቱ ካርሎስ፣ ባለፈው ሰኞ ፍርድ ቤት በቀረበበት ወቅት የሙያ መስክህ ምንድን ነው በሚል ከችሎቱ ለቀረበለት ጥያቄ፣ ብቁ አብዮተኛ ሲል ምላሽ ሰጥቷል፡፡ ዕድሜውን ሲጠየቅም፡- 17 ነው፤ ደስ ካላችሁ 50 አመት ጨምሩበት ሲል ያላገጠ ሲሆን  የተከሰሰበትን የወንጀል ድርጊት አለመፈጸሙን አስረድቷል፡፡
ካርሎስ ከ43 አመታት በኋላ የተከሰሰበትን የግድያ ወንጀል መፈጸሙን የሚያስረዱ 17 ያህል ምስክሮች በቀጣይ የምስክርነት ቃላቸውን እንደሚሰጡ የጠቆመው ዘገባው፤ የምስክሮችን ቃል የመስማቱ ሂደት በሁለት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ይጠናቀቃል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጧል፡፡
ከ23 አመታት በፊት በፈረንሳይ ልዩ ሃይል ክትትል በካርቱም በቁጥጥር ስር የዋለው ቬንዙዋላዊው አደገኛ ገዳይ ካርሎስ፤ በ1970 ዎቹ እና 80 ዎቹ በፈጸማቸውና ባስፈጸማቸው በርካታ የግድያ ወንጀሎች የእድሜ ልክ እስራት ተፈርዶበት ከዚያ ጊዜ አንስቶ በፈረንሳይ በእስር ላይ ይገኛል፡፡

የጋናው ፕሬዚዳንት ናና አኩፎ አዶ በአገሪቱ ታሪክ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሚኒስትሮችና ምክትል ሚኒስትሮች የተካተቱበትንና 110 ያህል ዕጩዎች የተካተቱበትን ዝርዝር ባለፈው ረዕቡ ይፋ ማድረጋቸው አነጋጋሪ መሆኑን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ይፋ ባደረጉት የዕጩ ሚኒስትሮች ዝርዝር የኢንፎርሜሽን ሚኒስቴርን ጨምሮ አምስት ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች እያንዳንዳቸው ሶስት ምክትል ሚኒስትሮች እንደሚኖራቸው የተገለጸ ሲሆን  የአገሪቱ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች “አዲሱ ሹመት የህዝቡን ገንዘብ የሚበሉ ሆዳሞችን ቁጥር ከማብዛት ባለፈ ፋይዳ የለውም” ሲሉ ሃሳቡን ተችተውታል፡፡
በርካታ ጋናውያን ፕሬዚዳንቱ ይህን ያህል ቁጥር ያላቸው ሚኒስትሮችን በዕጩነት ማቅረባቸውን በተለያዩ ድረገጾች እያጣጣሉት እንደሚገኙ የጠቆመው ዘገባው፤ የአገሪቱ የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር ሙስጠፋ ሃሚድ ግን፣ መንግስት በርካታ ሚኒስትሮችን መሾሙ የተያዘውን ሰፊ የልማት ዕቅድ በማስፈጸም ረገድ ትልቅ አቅም ይፈጥራልና ሊተች አይገባውም ብለዋል፡፡