Administrator

Administrator

       የምንመገባቸው ምግቦችና መጠጦች ለከፍተኛ ራስ ምታት (ማይግሪን) መንስኤ ሊሆኑ ይችላሉ። በራስ ምታት የመያዝ አጋጣሚዎች በተለያዩ ምክንያቶች (በአየር ፀባይ መለዋወጥ፣ በጠንካራ ሽታዎች፣ በከፍተኛ ብርሃን፣ በሌሎች በሽታዎች ሳቢያ፣ በካፌይን ሱሰኝነት ወዘተ) የሚያጋጥመን ቢሆንም የምንመገባቸው ምግቦችና ወደ አንጀታችን የምንልካቸው የተለያዩ መጠጦችም ለከፍተኛው ራስ ምታት (ማይግሪን) ሊያጋልጡን እንደሚችሉ የአሜሪካ ተመራማሪዎች አስታውቀዋል፡፡ ኔቸር በተሰኘው የምርምር ጆርናል ላይ ተመራማሪዎቹ ይፋ እንዳደረጉት፤የምንመገባቸው ምግቦች ከጭንቅላት ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያላቸው ታይራሚንስና ናይትሪ የተባሉ ኬሚካሎችን በስፋት ይይዛሉ፡፡ እነዚህ ኬሚካሎች ደግሞ የደም ዝውውር ሂደትን በማወክ፣ የራስ ምታትንና የዓይን አካባቢ ህመምን ያስከትላሉ፡፡
ሣይንቲስቶቹ በምርምር አረጋግጠናል ካሏቸውና ከፍተኛ የራስ ምታትን ያስከትላሉ በማለት ከዘርዘሯቸው የምግብና የመጠጥ ዓይነቶች መካከል የሚከተሉት ይገኙበታል፡፡
ቀይ የወይን ጠጅ
ቀይ ወይን ለራስ ምታት ህመም የሚያጋልጡ ኮንጀነርስና ታይራሚን የተባሉ ንጥረነገሮችን በብዛት ይይዛል፡፡ ስለዚህም ከሌሎች አልኮል መጠጦች ሁሉ የራስ ምታት ህመምን በማነሳሳት በእጅጉ ይታወቃል። የችግሩ ከፍተኛነት በወሰድነው የቀይ ወይን መጠንና በሽታን በመከላከል አቅማችን የሚወሰን ቢሆንም ቀይ ወይን መጠጣት ለከባድ የራስ ምታት ህመም የሚያጋልጥ መሆኑን አረጋግጠናል ሲሉ ተመራማሪዎቹ ገልፀዋል፡፡ ቀይ ወይን ለራስ ምታት ህመም እንድንጋለጥ የሚያደርገን በአልኮልነቱ ሳይሆን በነጭ ወይን ውስጥ የሌለና በቀይ ወይን ውስጥ ብቻ በሚገኘው ተፈጥሮአዊ ውህድ መነሻነት እንደሆነም እነዚሁ ተመራማሪዎች ጠቁመዋል፡፡  
ቸኮሌት
ቸኮሌትን አብዝቶ መመገብ ለከፍተኛ ራስ ምታት ያጋልጣል፡፡ በተለይም ጠቆር ያለውና ቡናማ ቀለም ያለው የቸኮሌት አይነት ህመሙን በማባባስ ለከፍተኛ ስቃይ የሚዳርግ መሆኑን የጠቆሙት ተመራማሪዎቹ፤ ከካካዋ ቅቤ የሚሰራው ነጭ ቸኮሌት ከራስ ምታት ህመም ጋር የሚያገናኘው ምንም ነገር አለመኖሩን በጥናታቸው ማረጋገጣቸውን ገልፀዋል፡፡
አይስክሬምና ሌሎች ቀዝቃዛ ምግቦች
እንደ አይስክሬም ያሉ በጣም የቀዘቀዙ ምግቦችን በምንመገብበት ወቅት በአፋችን ውስጥ የሚፈጠረው ከፍተኛ ቅዝቃዜ ለከባድ ራስ ምታት ያጋልጠናል፡፡ ለዚህም ምክንያቱ በአፋችን ውስጥ የተፈጠረው ቅዝቃዜ እስከ ጭንቅላታችን ድረስ ስለሚሰማን እንደሆነም አሜሪካዊያን ተመራማሪዎቹ ጠቁመዋል፡፡
ካፌን
ቡና እና ኮካ መሰል መጠጦች ውስጥ የሚገኘው ካፌን ሱስ የማስያዝ ባህርይ አለው። ይህንን መጠጣት በምናቆምበት ወይንም ሳንጠጣ በምንቆይበት ጊዜ ከባድ የራስ ምታት ህመም ያጋጥመናል፡፡ ካፌይን መውሰድ ያቆሙ ሱሰኞች ለድብርት ስሜት፣ ለመጫጫንና ለከባድ ራስ ምታት ህመም የተጋለጡ ናቸው፡፡ ካፌይኑ የአንጐላችንን ኤሌክትሪካል ሲስተም በማዛባት ሰውነታችን ተጨማሪ የቤታ ንዝረቶችንና አነስተኛ የቴታ ንዝረቶችን እንዲለቅ ያደርገዋል፡፡ ይህ ደግሞ በአንጐላችን ውስጥ የሚካሄደውን ኤሌክትሪካል እንቅስቃሴ በማዛባት ለከፍተኛ የራስ ምታት ህመም እንድንጋለጥ ያደርገናል፡፡
ካፌይን ነክ የሆነ መጠጦችን በጠዋት የመጠጣት ልምድ ያላቸው ሰዎች ካፌይኑ በሕብለ ሰረሰራቸው ውስጥ የሚገኙትን የደምቅዳ ቧንቧዎች በማጥበብ ደም በበቂ መጠን ወደ አንጐል እንዳይገባ ያደርጋል። በዚህ ሣቢያም ከባድ የራስ ምታት ህመም ያጋጥመናል ሲል ተመራማሪዎቹን ዋቢ አድርጐ ኔቸር ዘግቧል፡፡ 

Saturday, 30 January 2016 12:51

ካፌይንና እርግዝና

 ካፌይን ነክ የሆኑ ምግቦችና መጠጦች በእርግዝና ወቅት መውሰድ በፅንሱም ሆነ በእናቲቱ ጤና ላይ ጉዳት እንደሚያስከትል በጥናት መረጋገጡን Neurology የተሰኘ የህክምና ጆርናል ሰሞኑን ዘግቧል፡፡
ነፍሰጡር ሴቶች፤ የማነቃቃትና እንቅልፍን የማባረር ባህርይ እንዳለው የሚታወቀውን ካፌይን በሚወስዱበት ወቅት የልብ ምታቸውና የደም ግፊታቸው በከፍተኛ መጠን እንደሚጨምር   የጠቆመው ዘገባው፤በእናቲቱ ማህፀን ውስጥ የሚገኘው ፅንስም በፕላሴንታ አማካኝነት በሚደርሰው ካፌይን ሳቢያ የልብ ምቱ ሊዛባና ለአደጋ ሊጋለጥ እንደሚችል አመልክቷል።  በተጨማሪም ካፌይኑን አብዝቶ መውሰዱ በተደጋጋሚ ስለሚያሸና ነፍሰጡሯ ሴት ድርቀት እንዲያጋጥማትና ፅንሱ በቂ ፈሳሽ ለማግኘት እንዳይችል እንደሚያደርገው ዘገባው ጠቁሟል፡፡
አብዛኛዎቻችን ካፌይን የሚገኘው በቡናና በለስላሣ መጠጦች ብቻ ውስጥ ነው ብለን እናምናለን ያለው ዘገባው፤ ካፌይን በበርካታ የታሸጉ ምግቦች ውስጥም እንደሚገኝና እነዚህን ምግቦች አዘውትሮ መመገብ ለጤና እክል እንደሚያጋልጥ አመልክቷል፡፡ 

   በሸካ አካባቢ የሚኖሩ ብሔር ብሄረሰቦችን ባህላዊ ትውፊትና የአካባቢውን ተፈጥሮአዊ ውበት የሚያሳየውና የ22 ደቂቃ ርዝመት ያለው “ድብቁ የሸካ ደን ውበት” ዘጋቢ ፊልም ትላንት ምሽት በልዑል ሲኒማ ተመረቀ፡፡ የሸካ ዞን አስተዳደር ባህልና ቱሪዝም ቢሮ፣ መልካ ኢትዮጵያና የአውሮፓ ህብረት ሲቪል ሶሳይቲ ፈንድ በመተባበር የሰሩትን ይህን ፊልም፤ አርቲስት ዮሃንስ ፈለቀ ያዘጋጀው ሲሆን በብሉ ሚዲያ ፊልም ፕሮዳክሽን ተሰርቶ ቀርቧል፡፡ በምርቃቱ ላይ የአውሮፓ ህብረት ተወካዮች፣ የሸካ ዞን ኃላፊዎች፣ የመልካ ኢትዮጵያ አመራሮች፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና ጋዜጠኞች ተገኝተዋል፡፡

   22 አይነት የአገር ውስጥና የውጭ ቋንቋዎችን አቀላጥፈው በሚናገሩት አቶ ካሱ ሰቦቃ የተዘጋጀውና “ሳንታ ማሪያ” የሚል መጠሪያ የተሰጠው የመዝሙር ቪሲዲ ዛሬ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ በቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን አዳራሽ ይመረቃል፡፡ አቶ ካሱ በኦሮምኛ፣ በአማርኛ፣ በግዕዝ፣ በስፓኒሽ በፈረንሳይኛ፣ በጀርመንኛ፣ በግሪክ፣ በቻይንኛ፣ በአረብኛና በጣልያንኛ 11 መዝሙሮችን ያዘጋጁ ሲሆን 12ኛው መዝሙር 11ዱን በምልክት ቋንቋ የሚያሳይ እንደሆነ ታውቋል፡፡ “የቅዱስ ዳዊት በገና ከቅድስት ኢትዮጵያ በዓለም ቋንቋ ሲገለፅ” በሚል መርህ የተዘጋጀው የዚህ ቪሲዲ ዋና አላማው የቅዱስ ዳዊትን በገና ለዓለም ለማስተዋወቅና የኢትዮጵያን የቱሪዝም መስህብነት ለማሳየት እንደሆነ ዘማሪው ተናግረዋል፡፡ በቪሲዲው ምርቃት ላይ ሚኒስትሮች፣ የኤምባሲ ተወካዮች፣ የመገናኛ ብዙሀን ባለሙያዎች፣ አትሌቶችና አርቲስቶች እንደሚገኙም ተነግሯል፡፡ አቶ ካሱ አስተርጓሚ ከመሆናቸውም ባሻገር ታዋቂ ሼፍና አስጎብኚም እንደሆኑም ለማወቅ ተችሏል፡፡

የታዋቂው የሬጌ አቀንቃኝ የቦብ ማርሊ 71ኛ ዓመት የልደት በአል የዛሬ ሳምንት አርብና ቅዳሜ በተለያዩ የሙዚቃ ድግሶች በሻሸመኔ ከተማ እንደሚከበር አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡
በሙዚቃ ድግሱ ላይ ሲድኒ ሰልማንና ራስ ጃኒን ጨምሮ ከዛምቢያ፣ ሴራሊዮን፣ አሜሪካና ሌሎች አገራት የተውጣጡ 14 አርቲስቶችና ዲጄዎች እንደሚሳተፉበት ታውቋል፡፡
የቦብ ማርሊን የልደት በዓል ምክንያት በማድረግ የሚቀርበው የሙዚቃ ድግስ ዋና ዓላማው፤ በስሙ የተሰየመውን ትምህርት ቤት ጨምሮ ሌሎች ፕሮጀክቶችን ለማገዝ የሚያስችል ገቢ ለማሳሰብ እንደሆነ ተገልጿል፡፡
በአሉን አለምአቀፍ ለማድረግ የተለያዩ ጥረቶችን እያደረግን ነው ያሉት አዘጋጆቹ፤ የሬጌ አድናቂው ማህበረሰብ በድግሱ ላይ እንዲታደም ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡ 

Saturday, 30 January 2016 12:06

የኪነት ጥግ

(ስለ ማስታወቂያ)
የማስታወቂያ ኤጀንሲ 85% ማደናገርና 15% ኮሚሽን ነው፡፡
ፍሬድ አለን
ሸማቾችን እንዲገዙ ወይም እንዳይገዙ የሚወስነው የማስታወቂያህ ይዘት እንጂ ቅርጽ አይደለም፡፡
ዴቪድ ኦጊልቪ
ፊል ናይት እባላለሁ፡፡ በማስታወቂያ አላምንም፡፡
ፊል ናይት
መጽሔት ሰዎች ማስታወቂያ እንዲያነቡ የመገፋፊያ መሳሪያ ነው፡፡
ጄምስ ኮሊንስ
ማስታወቂያ የንግድ የደም ሥር ነው፡፡
ካልቪን ኩሊጅ
በኪነጥበብ ውስጥ ኃያሲው ብቸኛው ነፃ የመረጃ ምንጭ ነው፡፡ የቀረው ማስታወቂያ ነው፡፡
ፖሊን ካኤል
ማስታወቂያ ሃጢያት የሚሆነው መጥፎ ነገሮችን ሲያስተዋውቅ ብቻ ነው፡፡
ዴቪድ ኦጊልቪ
ማስታወቂያ ህጋዊ የሆነ  ውሸት ነው፡፡
ኤች ጂ ዌልስ
ማንም ያስተላለፍከውን ማስታወቂያ የሚቆጥር የለም፤ ሰዎች የሚያስታውሱት የፈጠርክባቸውን ስሜት ነው፡፡
ቢል በርንባች
ስለማስታወቂያ ግድ የሚሰጣቸው በማስታወቂያ ውስጥ የሚሰሩ ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡
ጆርጅ ፓርከር
ጥራትን ስጣቸው፡፡ ያ ነው ምርጡ የማስታወቂያ ዓይነት፡፡
ሚልተን ሄርሼይ
ማስታወቂያ የቢዝነስ ልሳን ነው፡፡
ጄምስ አር .አዳምስ
ራስህን የማታስተዋውቅ ከሆነ በሚወዱህ ጠላቶችህ ትተዋወቃለህ፡፡
አልበርት ሁባርድ
በማስታወቂያ የተዋጣለት ለመሆን ማስታወቂያ እንዴት እንደሚሰራ ማወቅ አያስፈልግም፡፡
ዊንስተን ፍሌቸር

  - በ48 ሰዓታት ለ50 ሚሊዮን፣ በ87 ቀናት ለ1 ቢሊዮን ጊዜያት ታይቷል

      እንግሊዛዊቷ አቀንቃኝ አዴል ባለፈው ጥቅምት ወር መጨረሻ የለቀቀችው “ሄሎ” የተሰኘ የሙዚቃ ቪዲዮ በዩ ቲዩብ ድረገጽ በአጭር ጊዜ ውስጥ በበርካታ ሰዎች በመታየት ረገድ “ጋንጋም ስታይል” በሚለው የደቡብ ኮርያዊው የፖፕ ሙዚቃ አቀንቃኝ ፒኤስዋይ ተወዳጅ ዜማ ተይዞ የቆየውን ክብረወሰን መስበሩ ተዘገበ፡፡
ዩ ቲዩብ ላይ በተለቀቀ በ48 ሰዓታት ውስጥ ለ50 ሚሊዮን ጊዜያት ያህል የታየው የአዴል “ሄሎ”፣ በ87ኛው ቀን  ላይም አንድ ቢሊዮን ተመልካቾች እንዳዩት የዘገበው አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ፤በ2012 የተለቀቀው “ጋንጋም ስታይል” በበኩሉ ይህን ያህል ተመልካች ሊያገኝ የቻለው በ160 ቀናት ጊዜ ውስጥ እንደነበር አስታውሷል፡፡
የአስር ጊዜያት የግራሚ ተሸላሚዋ አዴል፤ነጠላ ዜማውን ያካተተችበትና ባለፈው ወር ለገበያ ያበቃችው “25” የተሰኘ የሙዚቃ አልበሟም፣ በአሜሪካና በእንግሊዝ የሙዚቃ አልበም ሽያጭ ታሪክ በፍጥነት በብዛት በመሸጥ ክብረወሰን መያዙን ዘገባው አመልክቷል፡፡
በአለማችን የሙዚቃ ቪዲዮ ታሪክ በዩ ቲዩብ ድረገጽ ተለቅቀው ለአንድ ቢሊዮን ጊዜያት ያህል መታየት የቻሉት የሙዚቃ ቪዲዮዎች 18 ብቻ እንደሆኑም ተጠቁሟል፡፡

Saturday, 30 January 2016 11:59

የጸሃፍት ጥግ

(ስለ ክዋክብት)

- ምሽት ደስ ይለኛል፤ ጨለማ ከሌለ ክዋክብትን
ፈፅሞ ማየት አንችልም፡፡
ስቲፌኒ ሜዬር
- ድቅድቅ ያለ ጨለማ ሲሆን ክዋክብትን ማየት
ትችላላችሁ፡፡
ራልፍ ዋልዶ ኢመርሰን
- ክዋክብትን በተመለከተ የምናየው ሁሉ የድሮ
ፎቶግራፋቸውን ነው፡፡
አላን ሙር
- እጣፈንታችን ያለው በክዋክብቱ ውስጥ
አይደለም፤ በራሳችን ውስጥ እንጂ፡፡
ሊሳ ማንትቼቭ
- እያንዳንዱ ኮከብ በውስጥህ ያለውን እውነት
የሚያንፀባርቅ መስተዋት ነው፡፡
አበርጅሃኒ
- ክዋክብት የዩኒቨርስ ጠባሳዎች ናቸው፡፡
ሪኪ ማዬ
- ማታ ማታ እዚያ ላይ የሚታዩት ክዋክብት
ከምታስቡት የበለጠ ቅርብ ናቸው፡፡
ዶውግ ዲሎን
- ጨረቃን አትጠይቁ! ክዋክብት አሉልን!
ኦሊቭ ሂጊንስ ፕሮውቲ
- ጨረቃ ሙሉ በማትሆን ጊዜ ክዋክብት ይበልጥ
ደምቀው ያበራሉ፡፡
ምንጩ ያልታወቀ
- ጉድጓድን አልሞ ከመምታት ይልቅ ጨረቃን
አልሞ መሳት ይሻላል፡፡
ምንጩ ያልታወቀ
- ክዋክብት የዘላለም የጎዳና መብራቶች ናቸው፡፡
ሃሪት ቱብማን
- ለክዋክብት አልም፤ ሰማይን ልትነካ ትችላለህ፡፡
ኦኪው ማንዲኖ
- ሁላችንም ክዋክብት ልንሆን አንችልም፤
ሁላችንም ግን ብልጭ ማለት እንችላለን፡፡
ሔነሪ ዋድስዎርዝ ሎንግ ፌሎው

Saturday, 30 January 2016 11:55

የዘላለም ጥግ

• ጥያቄ የሚጠይቁ ሰዎች አያስፈሩኝም፡፡ እኔን
የሚያስፈሩኝ መልስ ለመስጠት አሻፈረን
የሚሉት ናቸው፡፡
ጃሶን ባቼታ
- ዓለም አገሬ ናት፤ የሰው ልጆች በሙሉ ወንድሞቼ
ናቸው፤ በጎ መስራት ሃይማኖቴ ነው፡፡
ቶማስ ፓይኔ
- የልጆቼን አይስክሬም 38 በመቶ እየበላሁባቸው
ስለግብር ምንነት አስተምሬአቸዋለሁ፡፡
ኮናን ኦ’ብሪን
- የጣልያን ምግብ የመብላት ችግሩ ከአምስት
ወይም ከስድስት ቀን በኋላ እንደገና ይርብሃል፡፡
ጆርጅ ሚለር
- በድጋሚ ሚስት ከማግባት ይልቅ የማልወዳትን
ሴት ፈልጌ አንድ የመኖሪያ ቤት እሰጣታለሁ፡፡
ሮድ ስቲዋርት
- ምንጊዜም ከጨለምተኛ ሰው ገንዘብ ተበደር፡፡
ገንዘቡ ይመለስልኛል ብሎ አይጠብቅም፡፡
ኦስካር ዋይልድ
- ችግሮችህን ፈፅሞ ለማንም አትንገር፡፡ 20 በመቶ
ያህሉ ግድ የላቸውም፤ 80 በመቶው ደግሞ
በችግር በመጠመድህ ደስተኞች ናቸው፡፡
ሎዮ ሆልትዝ
- ትዳር ከመያዜ በፊት ስለልጆች አስተዳደግ
ስድስት ኃልዮቶች ነበሩኝ፤ አሁን ስድስት ልጆች
አሉኝ፤ ነገር ግን ምንም ኃልዮት የለኝም፡፡
ጆን ዊልሞት
- የሰውን አዕምሮ ከመልሶቹ ይልቅ በጥያቄዎቹ
መመዘን ይቀላል፡፡
ፒሬ ማርክ
- ሁሉንም ውደድ፤ ጥ ቂቶችን እመን፤ ማ ንም ላ ይ
መጥፎ አታድርግ፡፡
ዊሊያም ሼክስፒር
- ሃቁን የምትናገር ከሆነ ምንም ነገር ማስታወስ
የለብህም፡፡
ማርክ ትዌይን
- ዘመዶቻችንን እግዚአብሔር ሰጥቶናል፤
እግዚአብሔር ይመስገን ጓደኞቻችንን መምረጥ
እንችላለን፡፡
ኢቴል ሙምፎርድ
- ጋራዥ ውስጥ መቆም መኪና እንደማያሰኝህ ሁሉ
ቤተክርስቲያን መሄድም ክርስቲያን አያሰኝህም፡፡
ቢሊ ሰንዴይ

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አባት ክፉኛ ይታመምና የአልጋ ቁራኛ ይሆናል፡፡ ባለቤቱ ቀደም ብሎ ህይወቷ አልፏል፡፡ ያለው አንድ ልጅ ብቻ ነው፡፡ የሚያስታምመውም እሱ ነው፡፡
በሰፈሩ በየምሽቱ የሚመላለስና በረት የሚያጠቃ አንድ ነባር ጅብ አለ፡፡ ሰው ሁሉ ይሄንን ጅብ ለመግደል ብርቱ ጥረት ያደርጋል፡፡ ሆኖም ሊገድለው የሞከረ ሰው ሁሉ በውጤቱ የሚናገረው አንድ ቃል ብቻ ነው፡፡
“እህ አያ እገሌ ያን ጅብ እንዴት አደረግኸው?” ይላል መንደሬው፡፡
አዳኙም፣
“አዬ! አድፍጬ አድፍጬ አመለጠኝ ባክህ!”
እንዲህ እንዲህ እየተባለ ያ ጅብ ግን በየማታው ከየበረቱ አንድ አንድ አህያና አንዳንድ ጊደር እየመነተፈ ጉልበቱ እየጠነከረ መጣ፡፡
ታማሚው አባትና ልጅም የዚሁ ጅብ ሰለባ እየሆኑ፣ ብዙ ከብት ከበረታቸው ተበልቶባቸዋል፡፡
አንድ ቀን አባትዬው ልጁን ጠርቶ፤
“ልጄ ሆይ”
“አቤት አባባ”
“የዚህን የጅብ ነገር አንድ መላ መምታት አለብን”
“ምን ዓይነት መላ አባዬ?”
“ወጥመድ ሰርተን እንይዘዋለን”
“ምን አይነት ወጥመድ?”
“ሄደህ ከመንደር ሙዳ ስጋ ገዝተህ ትመጣለህ”
“እሺ፤ ከዛስ?”
“ያንን ሙዳ ሥጋ በጠመንጃችን አፈ - ሙዝ ላይ ታስረዋለህ”
“እሺ፤ ከዛስ”
“ሙዳውን ያሰርክበትን ገመድ ጫፍ ጠመንጃው ቃታ ላይ ታስረዋለህ”
“ከዛስ?”
“በቃ ያንን ወስደህ በረታችን ፊት ለፊት ታስቀምጥለታለህ፡፡ አጅሬ ሥጋውን አገኘሁ ብሎ ሲጎትት ቃታውን ይስበዋል፡፡ ጥይቱ ባፉ ይገባና ድብን ያደርገዋል”
“እሺ አባዬ ዛሬ ማታ ያልከኝን አደርጋለሁ፤ ይሄ ከተሳካኮ የመንደሩ ህዝብ ነው የሚገላገለው፡፡ ለእኛም ጥሩ ስም ያተርፍልናል፡፡”
ልጅ በቃሉ መሰረት ሥጋውን ገዝቶ፣ ጠመንጃው ላይ አስሮ በረቱ ደጃፍ ላይ አስቀምጦ ይጠባበቅ ጀመር፡፡
ከሰዓታት በኋላ ልጁ ወደ አባቱ ሲሮጥ ይመጣል፡፡
“አባዬ አባዬ፤ ጉድ ሆነናል”
“ምነው? ምን ተፈጠረ” አለ አባት በድንጋጤ፡፡
“አባዬ፤ ጅቡ ጠመንጃውን በሰደፉ በኩል ነክሶ ሥጋውን ከነጠመንጃው ይዞት ሄደ፡፡”
አባትየውም፤
“ወይ ጉድ! እንኳን ጠመንጃ ሰጥተኸው እንዲሁም አልቻልነው!”
*          *          *
እንዲህ ያለ የሠለጠነ ጅብ አያድርስ ነው፡፡ ዛሬ በሀገራችን አያሌ የሰለጠነ ጅብ አለ፡፡ የሰለጠነ ጅብ መኖሩ ብቻ ሳይሆን የጅቦች ማሰልጠኛ ያለ ይመስል በርካታ ጅቦች መኖራቸው የበለጠ አሳሳቢ ያደርገዋል፡፡ ከዚህ እጅግ የከፋው ነገር ደግሞ የጅቦች የተጠላለፈ መረብ፣ በሜዳ ስሙ “ኔትዎርክ” የሚባል መኖሩ ነው፡፡ ጅብ ለማጥመድ የሚሞክሩት ጥቂት ናቸው፡፡ ስለሆነም በመረቡ ተጠልፈው ራሳቸው ይያዛሉ፡፡ የሙስናን ነገር ለመፍታት እጅግ አዳጋች ያደረገው ይሄ ነው፡፡ ከላይ ነገሩን ይከላከላሉ፣ እርምጃ ይወስዳሉ የተባሉት አካላት ጉዳዩ ውስጥ ካሉበት ነገሩ ሁሉ የግብር ይውጣ እንደሚሆን ግልፅ ነው፡፡ “ስለገብስ አታውራ፡፡ ፈረሱ እንዳይሰማ” ሆኗል ችግሩ፡፡ የምናጠምደው ወጥመድ ሁሉ ጠመንጃ የሚያስነጥቀን ከሆነ ገንዘቡ፣ ሀብቱ፣ መሬቱ ወዴት እንደሚሄድ ያለጥርጥር መናገር ይቻላል፡፡ ፈረንጆች who guards the guards ይላሉ፡፡ ተቆጣጣሪዎቹን ማን ይቆጣጠራቸዋል፤ ጠባቂዎቹንስ ማን ሃይ ይላቸዋል፡፡ እንደማለት ነው፡፡ የቢሮክራሲው፣ የሥራ አስፈፃሚውና የነጋዴው ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ዛሬ “ቢዝነስ” የሚባለው ቃል የተራው ዜጋ፣ የተራው ሟች (average mortal) ቋንቋ ሆኗል፡፡ የካፒታሊዝምን ሥርዓት መቀበል፤ “ነፃ ገበያ”፣ “የግል  ሀብት”፣ “የዲሞክራሲ ሥርዓት”፣ “የኢንዱስትሪ መስፋፋት”… እንደምንለው ቃለ-ተውኔት የቀለለ አይደለም፡፡
የካፒታሊዝምን ሥርዓት መቀበል “መሳም ወደሽ ጢም ጠልተሽ” ማሰኘቱ አይቀሬ ነው፡፡ የባህል ወረራው ታላቅ አደጋ ነው፡፡ In God we trust (በእግዚአብሔር እናምናለን) ከሚለው ዶላሩ ላይ ከተፃፈው መራሄ-ቃል ጀምረን (እንዲህ እያልሽ ውቴልሽን ሽጪ ይላሉ ወሎዎች) እስከ ታላላቅ የንግድ መቆጣጠሪያ ኮርፖሬት ኃይሎች ድረስ የተዘረጋ መረብ እንዳለ ማስተዋል አለብን፡፡ በዚህ መረብ ውስጥ የማይጠመደው ጅብ አለ፡፡ በምንም መልኩ ሰው ገለህም ቢሆን፤ ገንዘብ ያዝ የሚለው መርህ አለ፡፡ ከጋሪ እስከ መርከብ ነግደህ አትርፍ (እያጎ እንደሚለው “ገንዝብ ሰብስብ በተቻለ”) የሚለው አለ፡፡ ጉዳዩ ግን የአስርቱ ቃላት ግልባጭ ስብከት፣ ነው፡፡ ማለትም “ሥረቅ”፣ አመንዝር”፣ “የጓደኛህን ሚስት ተመኝ”፣ “ጎረቤትህን እንደራስህ አድርገህ ጥላ” ወዘተ ማለት ነው፡፡ የመንታፊዎች፣ የወሮበሎች፣ የመንገድ ላይ ጉልቤዎች፣ የታጣቂ ሰራቂዎች፣ የቁጭ በሉዎች፣ የምሁራዊ ሌቦች፣ የልማታዊ ቀማኞች፣ የአዛኝ - ቅቤ - አንጓች ዘራፊዎች፣ የረቂቅ አገር - ቦርቧሪዎች፣ የዓለም አቀፍ ጨረታ በዝባዦች፣ የባንክና የኢንሹራንስ መዝባሪዎች ወዘተ መፈልፈያ ነው ካፒታሊዝም፡፡ ታዲያ እነዚህ ፍልፍሎች እንደቃላት መጠሪያቸው የረከሱ አይደሉም፡፡ የክርስትና ስምም፣ የማዕረግ ጥምም፣ ሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ዕውቅና ያገኘ ስምም፣ የቢዝነስ ስምም፤ ያላቸው  የተከበሩ  ሥራዎች ናቸው። እንደኛ የተደላደለ ኢኮኖሚ በሌላቸው አገሮች ላይ እንግዲህ በእንቅርት ላይ ጆሮ  ደግፍ፣ በቡሃ ላይ ቆረቆር ማለት ነው፤ ካፒታሊዝም፡፡ ገንዘብና ገንዘብ እንጂ ሌላ ነገር  አታስቡ፡፡ እነሆ አምላካችሁ እሱና እሱ ብቻ ነው! ይላል መጽሐፈ - ንዋይ! ዕውቀት ባልበለፀገበት፣ ሃይማኖት በገንዘብ እየተሸረሸረ ባለበት፣ ባህልና ቅርስ ካንገት በላይ እየታሰበ ባለበት፣ አገም ጠቀም ፖለቲካዊ ኢኮኖሚ የሚያኮራ በሚመስልበት፣ የሚከበሩ በዓላት ሁሉ  የኛም እየመሰሉ በሚታዩበት፣ መሰረታዊ የሚባሉት ቤት፣ ውሃ፣ መብራት እንኳ በቅጡ በማይገኝበት አገር የካፒታሊዝም አባዜ ሲጨመርበት “እንኳን ጠመንጃ ሰጥተኸው እንዲሁም አልቻልነው” የሚያሰኝ ነው፡፡ ከዚህ ይሰውረን!