Administrator

Administrator

Saturday, 30 July 2016 12:35

የሥነ - ግጥም ሕይወት

ሥነ-ጽሑፍ ውስጥ ከተካተቱት ዘውጎች፣እጅግ ጥንታዊ ነው የተባለለት ግጥም፤ የእስትንፋሱ ክር፤ የዘመኑ ጥግ፤ ዞሮ ዞሮ ከጥንታዊያኑ ሀገራት ጋር መዛመዱ ግድ ነው፡፡ ለምሳሌ በቻይና ታሪክ ውስጥ እጅግ ጥንታዊውና በእጅጉ የተለመደው ስነ ጽሑፋዊ ቅርፅ ያለው ነው፡፡ በመሆኑም ከክርስቶስ ልደት በፊት ከ11ኛው ክፍለ ዘመን እስከ 6ኛው ክፍለ ዘመን ድረስ ያሉትን 305 ያህል ግጥሞች ያካተተው ‹‹The Book of ode›› ወይም የመውድሳዊ ግጥሞች መጽሐፍ የተባለው ጥራዝ በጥንታዊነቱ ይጠቀሳል። Guo Feng ወይም  Feng Falk songs, collected from chu-ci ሌላው የግጥም አይነት ነው፡፡ ይሄ የግጥም ዓይነት ደግሞ በቻይና እውነታዊነት /Realistic/ የተሠኘውን የግጥም- አይነት  ያስገኘ ነው፡፡ ፈቅ ሲል ደግሞ Li-Sao (ሊ-ሳኦ) ለቻይና ሮማንቲዝም- መንገድ ያበጀ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በስነ ጽሁፋዊ ልዕቀቱ ዘውድ የደፋ ነው፡፡
ይሁንና የታንግ- ዘመን መንግሥት የቻይና ወርቃማ ዘመን ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ግጥም መፃፍና ግጥምን በቃል ማነብነብ፣ ከቤተ መንግስት እስከ ተራው ሰው ጎጆ፤ ከዚያም አልፎ እስከ መሸታ (ሴተኛ አዳሪ ቤት) ድረስ የተለመደ ሆኖ ነበር፡፡ ሌላው ቀርቶ በግጥም የተዋጣለት ሰው፣ በዘመኑ የነበረውን የንጉሳዊ ቤተ መንግስት ፈተና እንኳን ባያልፍ ለአስተዳደር የመመረጥ ዕድል ነበረው፡፡
ሌላኛው የገጣሚያንና የግጥም መፍለቂያ የዕብራዊያን ሕዝብ ነበር፡፡ ዕብራዊያን አኗኗራቸው በአንድ ሥፍራ ያልረጋና በዘላንነት የሚተዳደሩ ነበሩ፡፡ የነርሱ ሥነ ጽሑፍ አፈጣጠሩ ከጨረቃ ፍቅርና ‹‹Sin›› ከተባለው የጨረቃ አምላክ ጋር የተያያዘ ነበር፡፡ በዘመኑም በግመሎቻቸው አንገት የሚያንጠለጥሉት ‹‹ስሉሴ›› የሚባለው የጨረቃ ቅርፅ፣ ከዚሁ ጋር የተያያዘ ነበር፡፡
የብሉይ ኪዳን የቅርፅና ሥነጽሑፍ ሃያሲያን (ፕሮፌሰሮች) በፅሁፍ እንዳስቀመጡልን፤በሲና በረሀ በሚጓዙበት ወቅት ቀን ቀን ለመጓዝ በረሀው-- አስቸጋሪ ስለነበር፤ የምሽቱን ጉዞ የተቃና ለማድረግ፣ የጨረቃን መውጣት መጠበቅ ግድ ነበር፡፡ ታዲያ ጨለማውን መጥላትና ጨረቃን መናፈቅ፤ በድንገት ለምትገለጠው ጨረቃ፤ ከስሜት የፈነዱ - ስንኞችን፤ ከሙዚቃና ዳንስ ጋር አቆራኝቶ አምጥቶታል፤ በማለት የግጥምን በታሪክ ውስጥ መወለድ ከፌሽታ ጋር ያቆራኙታል፡፡ አፈጣጠሩም የቡድን ነው የሚባለው ለዚህ ነው፡፡ የሥነ- ግጥም ምሁራን፤ ግጥም የመፃፍ የመጨረሻ ግቡ እርካታ ነው የሚሉንም ከዚህ የተነሳ ነው፡፡ ግጥም እንደዚህ ተፈጠረ ካልን፣ ከነዚህ ከተፈጠረባቸው ሁለት ሀገራት- ያንዱ በቅዱስ መጽሐፍ ተጠርዞ እናገኛለን። በተለይ ጥንታዊው የዕብራይስጥ ግጥሞች በአምስት አይነት ይከፈላሉ፡፡
 Lyric - ሙዚቃ-ንክር - አብዛኛው የዳዊት መዝሙር
Didactic - ከስሜት ይልቅ ዕውቀትና አእምሮ ላይ ያተኮረ
 Prophetic
Elegiac - የኤርምያስ ሰቆቃ - ሀዘንና ሙሾ
Dramatic - የኢዮብና የሰለሞን መዝሙር-በምልልስና በግለ መነባንብ (ሀሳቦችና እውነታዎች)
የመጽሐፈ ኢሳያስ ግጥሞች፤ በውበታቸው ከፍታ ከብሉይ መጻሕፍት የሚደርስባቸው የለም፤ በቃላት አጠቃቀምና በዘይቤዎች ሀብት የጠገበና ከፍ ያለ ነው፡፡
 ግጥም የስሜትና የሀሳብ ሃይል፣ በዜማ ተከሽኖ ወደ ሰዎች ጆሮና ልብ   የሚዘልቅ፤ የሚታይ ምናባዊ ሥዕል የሚሠራና ስልት ያለው የስነፅሑፍ ዝርያ ነው ማለት እንችላለን፡፡ የተመረጡ ሀሳቦች፣ በተመረጡ ቃላት ተገምደው በዜማ ጅረት ይፈስሳሉ፡፡ መነሻቸውም ስሜት ነው፡፡ ስሜት በራሱ ግጥም ነው ባንልም፣ ወደ ግጥም የሚነዳን ግን ስሜት ነው።
ታዲያ ግጥም በየዘመኑ የተለያዩ ክፍሎችና መደቦች  ይኖሩታል፡፡ አንዳንዶቹ በጀመሩበት ስያሜ ሲዘልቁ፣ ሌሎቹ በዘመንና በቦታ ለውጥ ስማቸውን በሌላ ስም ተክተዋል፡፡ ይሁንና ባለንበት ዘመን የግጥምን ዓይነቶች በሶስት እንከፍላቸዋለን፡፡
ተራኪ ግጥም፡- ቀላልና ወደ ተፈጥሮ የሚጠጉ፣ ገፀ ባህሪያትን ሊይዙ የሚችሉ
ሊሪክ ግጥም፡- ዜማዊ የሆኑና በስሜት የተሞሉ፣ መዝሙሮችና እንጉርጉሮዎች
ተውኔታዊ ግጥም፡-
በጥቅሉ ግጥም ሁለንተናዊ ቋንቋ፣ሰብዐዊ ስጦታና መግባቢያ ነው፡፡ ጥንታዊውም ሆነ ዘመናዊው ሰው፣ በየራሱ ዘመን ቅኝትና አውድ ይጠቀምበታል፡፡ በሁሉም ሀገር፣ በሁሉም ዘመን፣ ግጥም ይፃፋል ይደመጣል፡፡ በየትኛውም ሁኔታ፣ በየትኛውም ደረጃ ያለ ሰው ለግጥም ጆሮው ክፍት ነው፡፡ በገጠር ከሚኖረው ፊደል ያልቆጠረ እረኛና ወፍጮ ላይ መጅ ጨብጣ ካጎነበሰችው ልጃገረድ አንስቶ፣ በከተማ ከጥበቃ ሰራተኛው እስከ ዩኒቨርሲቲው ተመራማሪ ፕሮፌሰር ድረስ ከግጥም ውበት አያመልጡም፡፡ በቀጥታና በተዘዋዋሪ ያገኙታል፡፡ በሰርግ ቤት ዘፈን፣ በለቅሶ ስፍራ ሙሾ፣ በቤተ ክርስቲያን መዝሙር፣በቤተ መስጊድ መንዙማ ሆኖ ብቅ ይላል፡፡
ግጥም አራስ ቤት ያለን ህፃን ልጅ የሚያወዛውዘው ለምን ይሆን? … ብሎ መጠየቅ ግድ ነው፡፡ የገጣሚና የደራሲው ኤድጋር አላንፖ ብያኔ፣ ለዚህ መልስ የሚሰጥ ይመስለኛል፡- “…ግጥም ማለት … ሙዚቃ እርካታ ከሚፈጥር ሀሳብ ጋር ሲቀየጥ ነው፡፡ ቃላዊ ሙዚቃ፣ ፍካሬ፣ ምሰላና ዘይቤያዊ ቋንቋን አጣጥሞ የሚሰራ ነው፡፡” ይለናል።
ህፃናቱን የሚያወዛውዘው፣ ዜማው ነው፣ ምቱ ነው፡፡
ወደ ግጥም ውስጥ ገብተን - ልናየው ካሻን ደግሞ የጆን ዶኔን ሀሳብ እንመልከት፡- “የግጥም ሀሳብ ነፍስ ነው ካልን፣ የስንኞቹ ቴክኒክ ደግሞ አካሉ ነው፡፡” ሁለቱ አይነጣጠሉም፣ ማለቱ ነው፡፡
ግጥም በመላው ዓለም ያለው የጋራ መልክ ይህ ከሆነ፣ የአማርኛ ግጥሞችስ ዕድሜና ዕድገት የት ድረስ ነው? በርካታ ሰነዶች እንደሚነግሩን፤ የአማርኛ ስነ ግጥም ወረቀት ላይ ያረፈው /በፅሁፍ የቀረበው/ ከ14ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ ነው፡፡
*           *       *
ይህም ለንጉስ አምደፅዮን የተፃፈው ታሪካዊና የውዳሴ ግጥም ነው፡፡ የንጉሱን ተጋድሎ፣ የግዛቱን መስፋፋትና ጀግንነቱን የሚመለከቱ ግጥሞች ናቸው፡፡ እስከ 19ኛው ክፍለ ዘመን ድረስ በተመሳሳይ ሁኔታ ለአፄ ዳዊት፣ ለአፄ ይስሀቅ፣ ለአፄ ዘርዐ ያዕቆብ፣ ለአፄ ገላውዴዎስ /አጥናፍ ሰገድ/ የተገጠሙ ናቸው፡፡
የሃያኛው ክፍለ ዘመን መባቻ ግን የሀገሪቱ ኢኮኖሚና ማህበራዊ አቅጣጫ ከሰለጠነው ምዕራባዊ ዓለም ጋር ስለተጎዳኘ የአማርኛ ቋንቋም ከግዕዙ ይልቅ ስፍራ እያገኘ መጥቶ ነበር፡፡ በኋላም በቅድመ ፋሺስት ወረራ ጊዜ እነ ተስፋ ገብረሥላሴን የመሰሉ አገር ወዳዶች፣ የጣሊያንን ወረራ በመቃወምና ብሄራዊ ስሜትን ለመፍጠር ከፃፏቸው ጥቂት ግጥሞች በስተቀር ያን ያህል የተሻሻለ ግጥም አልነበረም፡፡ ነጋ ድራስ ተሰማ እሸቴ፣ ተክለሃዋርያት ተክለማርያም፣ ቀኝጌታ ዮፍታሄ - ከሚጠቀሱት ውስጥ ነበሩ፡፡
ዘመናዊ የአማርኛ ስነ ግጥም ዕድገት አሳይቷል የሚባልበት መነሻ ድንበር በድህረ ፋሽስት ወረራ  ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡ ዘመናዊ ትምህርትን ተከትሎ በሀገር ውስጥ የትምህርት መስፋፋትና የውጭ ሀገር ትምህርት ዕድሎች መከፈት፣ በቀጥታና በተዘዋዋሪ ይህ የጥበብ ዘርፍ እንዲያድግ ዋነኛውን ሚና ተጫውቷል፡፡
በዚህ ጊዜ የጀመረው የስነ ግጥም የተሻሻለ መልክ፣ እነ ከበደ ሚካኤልን የመሰሉ ገጣሚያንን ወልዶ ሀገሪቱን ከውጭው ዓለም ኪነ ጥበብና ሳይንስ ጋር ማገናኘት ችሎ ነበር፡፡ ከበደ ሚካኤል፤“የቅኔ ውበት”ን የመሳሰሉ ስራዎችን ይዘው ሲቀርቡ፣ መንግስቱ ለማም “የግጥም ጉባኤን” ይዘው ብቅ አሉ፡፡ በኋላ ደግሞ እነ ሰለሞን ዴሬሳ የዘመናዊውን ዓለም ሥነ ጽሑፍ ዝቀው በማምጣት፣ አዲስ አይነት ስልቶችን አስተዋወቁ፡፡ ይህንን ለውጥ አስመልክቶ መንግስቱ ለማ እንዲህ ብለው ነበር፡-
 “ባለንበት የስነ ጽሑፍ ዘመን ትልቅ ጥያቄ ቀርቦልናል፡፡ ጥያቄውን ለመመለስ የጥንታዊውን ስነ ግጥም ባህል ከዘመናዊው አቀራረብና የገለጻ ነፃነት ጋር አቀናጅተን አዲስ አይነት ውጤት መፍጠር ይጠበቅብናል፡፡ እጅግም ደግሞ በአዳዲስ የፈጠራ ሙከራ ተጠምደን፣ በየጊዜው በሚመጣው የፈጠራ አቀራረብ ንፋስ ስራችንን ነቅለን መጣልን ማስወገድ አለብን፡፡”
በተለይ ሰለሞን ዴሬሳ ግጥሞች አስተማሪና ሰባኪ መሆን የለባቸውም፣ ሲል ያመጣው አዲስ ሀሳብ፣ የጥበቡን ዓለም - የማሸበር ያህል አናግቶት ነበር፡፡ ከዚህም ሌላ ግጥም ምስጢር መሆን የለበትም ማለቱ አቤ ጉበኛን የመሳሰሉትን ደራስያን አላስደሰተም ነበር፡፡
ከዚህ በመቀጠልም ሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህንና ሰይፉ መታፈሪያን የመሳሰሉ ዘመናዊ ገጣሚያን መምጣት፣ በጥበቡ ዓለም ሌሎች ብርቅ ከዋክብትን የመጨመር ያህል ተቆጥሮ ነበር፡፡ በቋንቋ ልቀቱ ጣሪያ የነካው ፀጋዬና በቀላል ቋንቋ ሥዕል መሳል የሚችሉት ሰይፉ መታፈሪያ ጎን ለጎን ተቀመጡ፡፡

“ባለሀብቶቻችን ጭንቅላትንም ስፖንሰር እናድርግ››
   አቶ ቢንያም ከበደ የ“ንባብ ለህይወት” መሥራችና ሥራ አስኪያጅ ናቸው፡፡ ባለፈው ዓመት በሀምሌ ወር በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን
ማዕከል የመጀመሪያው የ“ንባብ ለሕይወት” የመጽሐፍትና የሚዲያ አውደ ርዕይ ተዘጋጅቶ ነበር፡፡ ዘንድሮም ባለፈው ሳምንት
ሁለተኛው ዙር የ“ንባብ ለሕይወት” የመጽሐፍት አውደ ርዕይ በተመሳሳይ ቦታ ተዘጋጅቶ ስኬታማ እንደነበር አቶ ቢንያም ለአዲስ
አድማስ ተናግረዋል፡፡ አውደ ርዕዩ መጻህፍት አሳታሚና ሻጮችን ጨምሮ በንባብና በትምህርት ዙሪያ የሚሰሩ በርካታ ተቋማት
የተሳተፉበት ነበር፡፡ ከአውደ ርዕዩ ጎን ለጎንም በርካታ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶች ተካሂደዋል፡፡ በግጥም፣በአጭር ልብወለድና በሌሎች
ሥነጽሁፋዊ ጉዳዮች ላይ ባለሙያዎች ጥናት አቅርበዋል፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ በ“ንባብ ለህይወት” ፕሮጀክት ዙሪያ፣የንባብ ባህልን ለማስፋፋት ምን ለመስራት
እንደታቀደ፣እንዲሁም በወደፊት ራዕዩና ተስፋው ዙሪያ ከአቶ ቢንያም ከበደ ጋር ተከታዩን ቃለ-ምልልስ አድርጋለች፡፡

 “ንባብ ለህይወት” እንዴት ተጠነሰሰ ?
የንባብ ጉዳይ የሚያስተናግዱና በዋነኝነት የሚሰሩ ተቋማት ቀደም ሲልም አሉ፡፡ ለምሳሌ ትምህርት ሚኒስቴር አንዱ ነው፡፡ ሌላው አንጋፋው የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር ከ50 ዓመት በላይ ሲሰራ ቆይቷል፡፡ በተለይ ባለፉት 10 እና 15 ዓመታት የንባብ ጉዳይ ስራዬ ብሎ ሲሰራ ነበር፡፡ በግልም ይህን ስራ የሚሰሩ አሉ፡፡ እነ ዳንኤል ወርቁን ብትወስጂ፡- ‹‹ኢትዮጵያ ታንብብ››፣ “አዲስ አበባ ታንብብ›› በሚል ከጀርመን የባህል ማዕከል ጋር በመተባበር ይሰሩ ነበር፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስም እንዲሁ በንባብ ላይ ይሰራል፡፡ በቅርቡ ደግሞ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴርም በንባብ ዙሪያ የሚያሰራቸው ስራዎች አሉ፡፡
በሌላ በኩል ግን ለንባብ ለህይወት መፈጠር ትልቅ ፈለግ የነበረው ‹‹አዲስ ጉዳይ መፅሔት›› አዘጋጅተው የነበረው ዓለም አቀፍ የመፅሀፍት አውደ ርዕይ ነበር፡፡ እነዚህ ተጠቃሽ ነገሮች እንዳሉ ሆነው፣ የኢትዮጵያ የንባብ ታሪክ ረጅም እድሜ ያስቆጠረ ቢሆንም ብቅ ጥልቅ እያለ እንጂ በወጥነት ሲሰራ አልነበረም ማለት ይቻላል፡፡ እኛ ይህንን ከፍተት ለመሙላት፣‹‹ንባብ ለህይወት›› የተባለውን ፕሮጀክት ይዘን ብቅ አልን ማለት ነው፡፡
በንባብ ደረጃ የሌላውን ዓለም ተመክሮ እንደ መነሻ ተጠቅማችኋል?
የአገራችንን የንባብ ጉዳይ ከጎረቤታችን ከኬንያ ጋር ብታወዳደሪ እንኳን በጣም ልዩነት አለን፡፡ ለምሳሌ በኬንያ ‹‹ካሪቡ›› የተሰኘ ትልቅ የመፅሐፍት አውደ ርዕይ አላቸው፡፡ በኬንያ ለአዋቂዎች ብቻ ሳይሆን ለህፃናትም ተብሎ ራሱን የቻለ አውደ ርዕይ ይዘጋጃል፡፡ የግብፅን ብንመለከት፣ከመቶ አመት በላይ ዕድሜ ያለው አውደ-ርዕይ አላቸው፡፡ ሀርጌሳ ብትሄጂ ኢትዮጵያዊም ጭምር የሚያስተባብሩበት የመፅሀፍት አውደ ርዕይ አለ፡፡ ወደ ደቡብ አፍሪካ ስንመጣ፣ በነፃነታቸው ማግስት አንዱን ግዛት ከሌላው የሚያገናኙበትና አንድ የሚሆኑበትን ነገር ሲፈልጉ የመጣላቸው የመፅሀፍት አውደ ርዕይ ነው። በየአመቱ በየግዛቱ የሚካሄድ ትልልቅ የመፅሀፍት አውደ ርዕዮች አላቸው፡፡
እኛ በሥነ ፅሁፍ ሀብታም የምንባል አገር ነን። በሀይማኖቱም ቢሆን በእስልምናውም ይሁን በክርስትናው ብዙ ያልተመረመሩ ግን ሊታዩ የሚገባቸው ድርሳናት ሞልተዋል፡፡ ከሀይማኖትም ውጭ በስነ እፅዋት፣በስነ ምህዳር፣ በስነ-ህንፃው ብዙ ያልተነኩ መፅሐፍት ስላሉን፣እነዚህን ይዘን ወደ አደባባይ መውጣት አለብን ነው አላማችን፡፡ ዋና አላማው፤ ያነበበ አዕምሮው የለማ ትውልድን መፍጠር ነው፡፡ ያነበበ የነቃ ሰው ሲወድሽም ሲጠላሽም በስሜታዊነት ሳይሆን በምክንያታዊነት ይሆናል፡፡ በሌላ በኩል ትውልዱ አንባቢ አይደለም፤እየተባለ ይነገራል፡፡ ለመሆኑ ለትውልዱ የተመቻቸ ነገር ፈጥረንለታል ወይ? በአመት አንድ ጊዜ በድንኳንና በመሰል ቦታዎች ለተወሰኑ ቀናት አውደ ርዕይ በማዘጋጀትና መፅሀፍ በመሸጥ ብቻስ ትውልዱን አንባቢ ማድረግ ይቻላል ወይ? የሚሉ ጥያቄዎችም አሉ፡፡ ንባብ ለህይወት ይህንን ጥያቄ በተቻለ መጠን ለመመለስ እየተጋ ነው፡፡
በምን መልኩ?
በጣም ጥሩ፡፡ ንባብ ለሕይወት ሲዘጋጅ መፅሀፍት ብቻ አይደለም የሚሸጡት፡፡ የተለያዩ ለትውልዱ ግንዛቤ የሚፈጥሩ ትምህርቶች ሴሚናሮች፣ ጥናታዊ ፅሁፎች፣ የልጅ አስተዳደግ ስልጠናዎች ተዘጋጅተው ነበር፡፡ ይህ ለምን ሆነ? አንብቡ ከማለት በፊት ምን አይነት መፅሀፍ ማንበብና እንዴት መነበብ  እንዳለበት ቅድሚያ ግንዛቤ መፍጠር ስለሚያስፈልግ ነው። በንባብ ለህይወት ብዙ ክንውኖች አሉ፡፡ በተለይ የሰሞኑ ማለትም ሁለተኛው የንባብ ለህይወት አውደ ርዕይ ከተጠበቀው በላይ ውጤታማ ነበር። በዚህ ፕሮግራም ብዙዎች የተደሰቱበት፣ብዙዎች ጥያቄያቸው መልስ ያገኘበት ነው፡፡ ንባብ ለሕይወት የተመሰረተውም አንተነህ ከበደ፣ እኔ፣ እስክንድር ከበደ፣ ጥበቡ በለጠና ሳምሶን አመሀ ተሰበሰብንና እስኪ ይህንን ነገር እንስራ፤አንድ የሚያደርገን ነገር ነው አልን፤ውጤማ ሆነ፡፡
ለአውደ ርዕዩ ሀምሌ ወር የተመረጠበት ምክንያት ምንድን ነው?
ሀምሌ የተማሪዎች መደበኛ ትምህርት የሚዘጋበትና ብዙ ተማሪዎችና ወጣቶች ፋታ የሚያገኙበት ወቅት ስለሆነ ነው የተመረጠው። ዘንድሮም ሀምሌ የሆነው ለዚህ ነው፤ በዚሁ ይቀጥላል፡፡ ስለዚህ ተማሪዎች ከትምህርት ውጭ ሁለገብ እውቀት የሚያገኙበት ዕድል ይፈጥራል ማለት ነው፡፡
በአውደ ርዕዩ ላይ ከመፅሐፍት ነጋዴዎች ሌላ የተሳተፉት እነማን ናቸው?
አውደ ርዕዩ የተለያየ አይነት እውቀትና እሳቤ እንዲንሸራሸርበት የታሰበ በመሆኑ በርካታ ወገኖች እንዲሳተፉ ማድረግ ዋነኛ አላማው ነበር፡፡ ስለዚህ የምርምር ተቋማት፣ ለምሳሌ ስራ አመራር ኢንስቲቲዩት፣ ቅድስተ ማሪያም ዩኒቨርሲቲ፣ አልታ የስልጠና ማዕከል፣ ትምህርት ሚኒስቴርና ትምህርት ቢሮዎች በተቋም ደረጃ ምን እየሰሩ ነው የሚለውን ይዘው እንዲወጡ ተደረገ፡፡ በሌላ በኩል የእምነት ተቋማትም እንዲሁ በክርስትናውና በእስልምናው ያሉ፣የበለጠ አስተምህሯቸውን በንባብ ላይ ያደረጉትን ይዘው እንዲቀርቡ አቅደን ይሄ ተሳክቶልናል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ-ክርስቲያን፣ ማህበረ ቅዱሳን፣ ቅድስት ማሪያም ገዳም፣ የጆቫ ዊትነስ (የሁዋ ምስክሮች)፣ የፕሮቴስታንት አማኞች፣ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን፣ በእስልምናም አልነጃሺ፣ አልተውባና አላክሳ የተባሉ የእምነት ተቋማት ድርሳኖቻቸውን፣ ዶክመንቶችንና መፅሐፍት በበቂ ሁኔታ ይዘው ቀርበዋል፡፡ እነዚህን የእምነት ተቋማት በአንድ ቦታ በማድረግ ያሏቸውን የንባብ ባህሎች ልምድ እንዲለዋወጡና እንዲወያዩ አድርገናል፡፡ ‹‹የእምነት ተቋማትና የንባብ ባህላቸው ምን ይመስላል›› የሚል ፕሮግራም በማዘጋጀት ምሁራኖቻቸው ሀሳባቸውን ለታዳሚ አካፍለዋል፡፡ ለምሳ ዶ/ር መሀመድ ዘይን በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአረቢክ ዲፓርትመንት መምህር፤በእስልምናው ልክ እንደ ቆሎ ተማሪ ያለው፣ ‹‹መደርሳን›› ስለሚባለውና ለዘመናዊ ትምህርት ስላለው አስተዋፅኦ ሰፊ ትንታኔ ሰጥተዋል፡፡ በኦርቶዶክስ በኩል መጋቢ ሀዲስ እሸቱ አለማየሁ፣ እነ ዶ/ር መጋቢ ሀዲስ ሮዳስ ታደሰ፤ የእምነት አስተምህሮቶች ለንባብ ባህላችን ስለሚያበረክቱት አስተዋፅኦ ጥሩ ጥሩ ትንታኔዎችን አቅርበዋል፡፡
የአልታ የማማከር አገልግሎት ባለቤትና የስነ-ልቦና ባለሙያው ዶ/ር ወንድወሰን ተሾመ፣ ዶ/ር ወዳጄነህ ማህረነም ጥናታዊ ፅሁፍ አቅርበው ነበር። እንዴት እናንብብ፣ ምን እናንብብ በሚል ስለ ቅድመና ድህረ ንባብ፣ አንድን መፅሀፍ እንዴት መቼ ብናነበው ውጤታማ እንሆናለን በሚለው ላይ ፅሁፍ አቅርበዋል፡፡ ለምሳሌ በዶ/ር ወዳጄነህ ጥናት ላይ በቻይና አገር በዓመት ውስጥ ከግማሽ ሚሊዮን በላይ መፅሐፍት ታትሞ፣ ህይወት አጭር በመሆኑ ላለን ለምንቆይበት ህይወት ጠቃሚውና ቅድሚያ ተሰጥቶ ልናነብ የሚገባው የትኛው አይነት ነው የሚለው ላይ ጥልቅ ጥናታዊ ፅሁፍ አቅርበዋል፡፡ ይሄን ስትመለከቺ አውደ ርዕዩ መፅሐፍት የሚሸጥ የሚለወጥበት ብቻ ሳይሆን ብዙ እውቀትና ትምህርት፣ የልምድ ልውውጥ የሚገበይበት ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ብዙ ተደክሞበታል፡፡
ንባብ ለህይወት ላይ የሚሳተፉ የመፅሐፍት አቅራቢዎች የዋጋ ቅናሽ እንዲያደርጉ ይገደዳሉ የተባለው እውነት ነው?
እውነት ነው ይገደዳሉ ብቻ ሳይሆን ለመሳተፍም ዋነኛ መሰፈርት ነው፡፡ ታዲያ የዋጋ ቅናሹ በስም ብቻ በመናገር ብቻ ሳይሆን እውነተኛ ቅናሽ  ነው። ምን ለማለት ነው----አንዳንዴ የበዓል ባዛር ላይ ህብረተሰቡ የዋጋ ቅናሽ አገኛለሁ ብሎ ሲሄድ እቃው ጭራሽ ገበያ ላይ ከሚሸጠው በጣም ተወድዶና ተጋንኖ ያገኘዋል፤ ግን የዋጋ ቅናሽ እንዳለ ይነገራል። በንባብ ለሕይወት ላይ እንዲህ አይነት ነገር የለም። በዚህ ዓመት ላመሰግን የምወደው ቡክ ላይት እና ቡክ ወርልድ ከ10 እስከ 80 በመቶ ቅናሽ በማድረግ፣ ለህብረተሰቡ ትርጉም ያለው ስራ ሰርተዋል፡፡
እስኪ መጻህፍት በሶፍት ኮፒ በነፃ ሲሰጡ ስለነበሩበት ሁኔታ አስረዱኝ? ምን ያህል መፅሐፍቶችን ለታዳሚ ሰጣችሁ?
የዘንድሮ የንባብ ለህይወት ትልቁ ውበትና መልካም ገፅታ ደግሞ የነዚህ ቀሊለ መፅሐፍት (ኢ-ቡክ) ጉዳይ ነው፡፡ ሰው የግድ በመፅሐፍ መልክ ተጠርዞ ማንበብ የለበትም፤ባገኘው አጋጣሚና በሚመቸው መንገድ እንዲያነብና እንዲበረታታ ማድረግ ተገቢ ነው ብለን አሰብን፡፡ የዛሬ ዓመት ከኢትዮጵያ እውቀትና ቴክኖሎጂ ሽግግር ማህበር እንዲሁም ከቡክ ኤይድ ኢንተርናሽናል፣ ከቡክ ፎር አፍሪካ ጋር በመተባበር አንድ መቶ ሺህ ኢ-ቡኮችን በተለይም የትምህርት መፅሀፍቶች ላይ ትኩረት አድርገን በማቅረብ በነፃ ሰጥተን ነበር፡፡ በጣም የሚገርም ግብረ መልስ ነበር ከማህበረሰቡ ያገኘነው፡፡ ይህን መነሻ አድርገን ዘንድሮ ግማሽ ሚሊዮን ኢ-ቡኮችን  አመጣን፡፡ ወደ 40 የሚሆኑ ኮምፒዩተሮችን ደርድረን  ፈቃደኛ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን የዳታ ቤዝ አደራደሩን እንዲያግዙን በማድረግና በየዘርፉ መፅሐፍቱን በመከፋፈል ጎብኚ በቀላሉ በፍላሽ፤ በሀርድ ዲስክ፣ በሲዲ ይዞ እንዲሄድ አደረግን፡፡ ይሄ ለእኛ ትልቅ ስኬት ነው፡፡ እዚህ ጉዳይ ላይ በቀጣይ ከኢትዮጵያ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ጋር የምንሰራቸው መርሀ-ግብሮች አሉ፡፡
ምን አይነት መርሀ ግብሮች ናቸው?
የሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ በአብይ መሀመድ በመክፈቻው ላይ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር፤ በኢትዮጵያ ስነ-ፅሑፍ ውስጥ እነ ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን ያበረከቱትን አስተዋፅኦ አንስተው፣ ንባብ ለህይወት የተባለው ፕሮጀክት በተለይ በኢ-ቡኮች ላይ አብሮን እንዲሰራ እንፈልጋለን ብለዋል፡፡ ሰው በአመት አንዴ በሚዘጋጅ አውደ ርዕይ ላይ ብቻ መፅሐፍ መውሰዱ ቀርቶ መፅሐፍቶች እንደ ልብ የሚያገኝባቸው ካፌዎች እንዲቋቋሙ የሚል ነው፡፡ እኛም በዚህ ላይ የያዝነው እቅድ ስለነበር በቀጣዩ ዓመት ተግባራዊ ይደረጋል፡፡
የንባብ አምባሳደሮችን መርጣችኋል አይደል?
ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ የመፅሐፍ አውደ ርዕይ እከሌ ሀሳቡን አመጣው፣ እከሌ ጠነሰሰው የሚባል አይደለም፤ ሁሉም የራሱ መነሻ አለው። በጭውውታችን መነሻ ላይ የነገርኩሽ ግለሰቦችና ድርጅቶች መነሳሳትና እንቅስቃሴ በእኛ ላይ የፈጠረው በጎ ተፅዕኖ፣ ‹‹ንባብ ለህይወት››ን ይዘን እንድንመጣ አድርጎናል፡፡ ስለዚህ አውደ ርዕዩን በዓመት አንዴም ሁለት ጊዜም ከዚያም በላይ ማካሄድ ይቻላል፤ነገር ግን ንባብ የዕለት ከዕለት የህይወት አካል እንዲሆን ካስፈለገ በተለይ በትምህርት ተቋማት ላይ መሰራት አለበት፡፡ ስለዚህ ይህን ስራ የሚያስቀጥሉ የንባብ አምባሳደሮች ከተለያየ የሙያ ዘርፍ መርጠናል። እነዚህ ሰዎች የበቁ አንብበው የጨረሱ፣ ከዚህ በኋላ ምሳሌ ይሆናሉ ማለት ሳይሆን ለንባብ ፍቅር ያላቸው፣ በሙያቸው ቢናገሩ የሚደመጡ ናቸው ያልናቸውን መርጠናል፡፡ ለምሳሌ ከስነ-ፅሁፍ ጋዜጠኛ ጥበቡ በለጠ፣ በእውቀቱ ስዩምና አለማየሁ ገላጋይን ይዘናል፡፡ በስነ- ጥበብ (ስዕሉ) አካባቢ ደግሞ ረዳት ፕ/ር በቀለ መኮንን መርጠናል። በትምህርት ዘርፉ ደግሞ የመጀመሪያዋ የባዮሎጂ ሴት ፕሮፌሰር በኢትዮጵያ የዓለምፀሀይን ስንመርጥ፣ የማነቃቃት ስራ ከሚሰሩ ደግሞ የትነበርሽ ንጉሴን ይዘናል፡፡ በስራ በአመራር በኩል የናሽናል ኦይል ኩባንያ ስራ አስኪያጅ የሆኑትን አቶ ታደሰ ጥላሁንን መርጠናል፡፡ አቶ ታደሰ ጥላሁን በተለይ በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ለንባብ በሚደርጓቸው ንግግሮች ነው የሚታወቁት። ከስፖርቱ ሰውነት ቢሻው፣ ከትወናው ግሩም ኤርሚያስ በአምባሳደርነት ተመርጠዋል። 97 ያህል ቤተ- መፅሐፍትን በገጠሪቱ የአገራችን ክፍል በማቋቋም ከኦክስፋም ካናዳ ጋር ትልቅ ስራ የሰራችው ማህሌት ሐይለማሪያምም ተመርጣለች። እነዚህ ሰዎች ስራዎቻቸውን መስራት ይጀምራሉ፡፡
በዋናነት የአምባሳደሮቹ ስራ ምንድን ነው?
ባለፈው ዓመት ከት/ቤቶች ጋር የተለያዩ ውጣ ውረዶች ስለገጠሙን በአምባሳደሮች በኩል ብዙ ስራ ሰርተናል ማለት አንችልም፡፡ ዘንድሮ ግን እሁድ ዕለት በተካሄደው የመዝጊያ ስነ ስርዓት ላይ ሁሉንም የትምህርት ቢሮዎችና የትምህርት ተቋማት አምባሳደሮቻችን፤በየት/ቤቱና በየተቋማቱ እየሄዱ ስለ ንባብ ያላቸውን ተሞክሮ እንዲያካፍሉ፣ ስለ ንባብ እንዲሰብኩ እንዲፈቀድላቸው ቃል አስገብተናል፡፡ ከመፍቀድም ባለፈ ተቋማቱ የመፅሐፍ አበርክቶት እንዲያደርጉም እንደሚነግሯቸው ሃላፊዎቹ ቃል ገብተዋል፡፡ ይህ ቃል ሲገባልን አለማየሁ ገላጋይ፤ ‹‹እስካሁን የምንመክተው በዱላ ነበር፤ አሁን ጠብመንጃውን ሰጥታችሁናል›› ነው ያለው። ከ2009 ዓ.ም ጀምሮ አምባሳደሮቹ በየቦታው እየሄዱ ያስተምራሉ፤ ተሞክሯቸውን ያካፍላሉ፡፡ ይህ የሚሆነው ዓመቱን ሙሉ ነው፡፡ ምን እንደሰሩ ሪፖርት ያደርጋሉ፤ ይገመገማሉ፡፡ ይህን እየጨመቅን ለሶሻል ለኤሌክትሮኒክስ፣ ለህትመት ሚዲያው እናሰራጫለን፡፡ በሚዲያ በኩል ድሬ ቲዮብ፣ የኛ ቲዩብ፣ አዲስ አድማስ፣ ቁምነገር መፅሄት፣ ኢቢኤስ፣ ሸገር ኤፍኤም፣ ናሁ ቴሌቪዥንና ሌሎችም አብረውን እየሰሩ ነው፡፡ እናመሰግናለን፡፡ ይሄ የሁሉም ትብብር ያለበት በመሆኑ ለውጥ ያመጣል የሚል ከፍተኛ እምነት አለን፡፡
በልጆች በኩል ትኩረት የምታደርጉበት ሌላ ፕሮግራም አለ?
አዎ ‹‹ንባብ ለህይወት ንባብ ለልጆች›› የተባለ ፕሮጀክት አለን፡፡ ይህ ፕሮጀክት ልጆችን እያዝናናን ንባብ እንዲያፈቅሩ የምናደርግበት ነው፡፡ ለዚህም ሙዚቃ የተደረሰላቸው ተረቶች ይኖራሉ፡፡ ይህንን በሁለተኛው ንባብ ለህይወት፣ በአራቱም ቀናት ሙያተኞች እየጋበዝን ሰርተንበታል፤በጣም ጥሩ ምላሽ አግኝተንበታል፡፡ ከአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ ጋር ተነጋግረን፣ ከመጪው አመት ጀምሮ ታች ድረስ በመውረድ፣ በልጆቹ ላይ ለመስራት ስምምነት ላይ ደርሰናል፡፡
በየኮንዶሚኒየምና በየሪል እስቴቶቹ የማንበቢያ ስፍራ ለመፍጠር ስለማቀዳችሁ ሰምቻለሁ፡፡ እስቲ ያብራሩልኝ ?
ንባብ ትልቁ ችግር ነው ብለን የምናስበው፣በአቅራቢያችን የንባብ ማዕከል አለመኖሩ ነው፡፡ በየኮንዶሚኒየም ቤቶች ቤተ-መፅሐፍት የሉም ግን እንዳለመታደል ሆኖ መጠጥና ጫት ቤቶች ይበዛሉ፡፡ ይህንን የምንቀይረው አማራጮች በማቅረብ ነው፡፡ በየክ/ከተማውና በየወረዳው አዲስ አበባ ውስጥ ከ80 በላይ ወጣት ማዕከላት አሉ፤ግን ምን ያህል በትጋት ይሰራሉ የሚለውም ሌላ ጥያቄ ነው፡፡ ወጣቱን ወደ ንባብ ለማምጣት እንደ እቅድ የያዝነውና ከሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ጋር እየተነጋገርን አዎንታዊ ምላሽ ያገኘንበት ጉዳይ በየኮንዶሚኒየም ቤቶቹ ግቢ አነስተኛና ተንቀሳቃሽ የሆኑ የመፅሐፍ ማንበቢያ ቦታዎችን መፍጠር ነው፡፡ ለዚህም ፕሮጀክት ብሪቲሽ ካውንስል ከፍተኛ የመፅሐፍት ድጋፍ ሊያደርግልን ስምምነት ተፈራርመናል፡፡ ከአገር ውስጥ ደግሞ ሜጋ፣ ስፖትላይት፣ አስቴር ነጋ ኣታሚ፣ ቡክ ወርልድና ቡክ ኮርነር ያሉት ድርጅቶች እገዛ ለማድረግ ቃል ገብተዋል፡፡ በቀጣይ ዓመት እነዚህን ድጋፎች በማሰባሰብ፣በሙከራ መልክ በተወሰኑ አካባቢዎች እንተገብራለን፡፡
በ2ኛው ንባብ ለህይወት ምን ያህል ተሳታፊዎች መፅሐፍት አቀረቡ? ከባለፈው አመትስ ጋር ሲነፃፀር በምን ያህል ጨመረ? የጎብኚውስ ሁኔታ እንዴት ነበር?
እውነት ለመናገር ብዙ ተስፋ እያገኘንበት ያለ ትልቅ ፕሮጀክት ነው፤ ንባብ ለሕይወት። በጎብኚ ብዛት፣ በተሳታፊ ቁጥር፣ በጎብኚም አይነት እጅግ የተደሰትንበት ነው የዘንድሮው። አምና 117 ተሳታፊዎች ነበሩ፤ ዘንድሮ 132 ድርጅቶች ተሳትፈዋል፡፡ ባለፈው አመት 62 ሺህ ጎብኚዎች ነበሩ፤ ዘንድሮ ከ83 ሺህ ሰው በላይ ጎብኝቶናል፡፡ በአስተያየት መስጫ ደብተሮች ላይ እንዳየነው፣ከተለያዩ ሙያ ተቋማት የመጡ ብዙ አይነት ህዝቦች ጎብኝተዋል፡፡ ይሄን ያህል ባልልሽም እጅግ ብዙ መፅሐፍት ተሸጠዋል፡፡ የዋጋው ቅናሽ አቅም አጥቶ ከማንበብ የተገታውን ህዝብ መልሶ አምጥቶታል፡፡ ወደፊትም ወደ ንባብ ይመልሰዋል የሚል እምነት አለን፡፡
 ንባብ ለህይወት ከአዲስ አበባ የመውጣት ዕቅድ የለውም?
 ስንጀምር ከአዲስ አበባ ነው፤ ግን ተጓዥ እንዲሆን እንፈልጋለን፡፡ ኤግዚቢሽኑ እንደ ንግድ መታሰብ አለበት፡፡ ብዙ ወጪ አለው፤ የአዳራሽ ኪራይ የማስታወቂያና የሎጅስቲክ ብዙ ወጪዎች አሉ፡፡ ይህንን የሚሸፍኑ ያገባኛል የሚሉ ባለሀብቶች ያስፈልጉናል፡፡ መጋቢ ሀዲስ እሸቱ አለማየሁ በመዝጊያ ስነስርዓቱ ላይ፤‹‹የእግር ኳስ ፕሮግራሞችን በሬዲዮ ስፖንሰር ለማድረግ ብዙ ድርጅቶች ሲሻሙ እሰማለሁ፤ እግር ኳስን ስፖንሰር ማድረግ እግርን ሰፖንሰር እንደማድረግ ነው፤ባለሀብቶቻችን ጭንቅላትንም ስፖንሰር እናድርግ›› ሲሉ አሳስበዋል። አቅም ሲጎለብት፣ ስፖንሰር ስናገኝ በየክልሉ ንባብ ለህይወት ይንቀሳቀሳል፡፡
ፕሮግራሙ ምን ያህል ወጪ አስወጣችሁ?
ወረቀት ላይ የሰፈረውን መናገር ይቻላል፤ከ800 ሺህ ብር በላይ ወጥቶበታል፡፡ ግን ጥንታዊ ፅሁፍ ሳይከፈላቸው ያቀረቡ ምሁራን በጉልበትና በሙያ ያገዙንን እንዴት በገንዘብ እንተምነው? ምንስ ያህል ነው ዋጋው? ትልቅ አቅም የጠየቀ፣ ብዙ እውቀት የፈሰሰበት ነው፡፡
ዘንድሮ ማንን ነው የሸለማችሁት?
በመጨረሻው ቀን ኢ/ር ታደለ ብጡልንና ተስፋ ገ/ስላሴን ባበረከቱት አስተዋፅኦ ሸልመናቸዋል፡፡
በእያንዳንዱ ቀን አዳዲስ መፅሐፍት በመመረቅ ነበር ፕሮግራም የምትከፍቱት ስንት መፅሐፍ ተመረቀ
በርካታ መፅሀፍት ተመርቀዋል ይሄ ባህል ይቀጥላል ብዙ መልካም ግብረ መልስም አግኝተንበታል፡፡



በባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ከመምህርነት እስከ ፕሬዚዳንትነት ባገለገሉት ዶ/ር ፀሀይ ጀንበሩ የተፃፈውና በፀሀፊ ግላዊ ህይወትና ገጠመኝ ላይ የሚተኩረው ‹‹የአንጎሌ ሁካታ›› መፅሀፍ ገበያ ላይ ዋለ፡፡
አንድ ሰው ግለታሪኩን በዚህ መልኩ ሲፅፍ በአይነት የመጀመሪያው ነው የተባለለት ይሄው መፅሀፍ ከራስ ገጠመኝ በመነሳት ማህበራዊ ችግሮችን ከስነ- ልቦና አንፃር የሚተነትን ነው ተብሏል፡፡ በ455 ገፅ የተዘጋጀው መፅሀፉ በ125 ብር ለገበያ የቀረበ ሲሆን ዶ/ር ፀሐይ በ1993 ዓ.ም ‹‹ደመላሽ›› የተሰኘና ስድስት አጫጭር ታሪኮችን የያዘ መፅሀፍ ለንባብ ማብቃታቸው ይታወሳል፡፡

የደራሲ በላይ ደስታ ስራዎች የሆኑት “የአበው አንደበት” እና “ያልተነበበው መፅሀፍ” የተሰኙ መፅሀፍቶች ከነገ በስቲያ በብሄራዊ ቴአትር አዳራሽ ከቀኑ 11፡00 ሰዓት ጀምሮ ይመረቃሉ፡፡ “የአበው አንደበት” የተሰኘው መፅሀፍ አንድ ሰው ለራሱ፣ ለቤተሰቦቹ፣ ለጓደኞቹና ለማህበረሰቡ በጎ ምክርን የሚለግስ እንደሆነና በሁሉም ጉዳይ ዙሪያ ጥልቅ ሀሳቦችን መሰብሰቡ የተለገፀ ሲሆን ከ90 በላይ በሆኑ ታላላቅ አባቶች የተነገሩ ከሶስት ሺህ በላይ ጥቅሶች፣ አባባሎችና ፍልስፍናዎች ተካትተውበታል ተብሏል፡፡ መፅሀፉ በ242 ገፆች ተመጥኖ፣ በ70 ብር ከ90 ሳንቲም ለገበያ የቀረበ ሲሆን ሁለተኛው ተመራቂ “ያልተነበበው መፅሀፍ” በ226 ገፆች ተመጥኖ በ69 ብር ከ50 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡፡ ደራሲው ከዚህ ቀደም ‹‹የስለላ ጥበብ››፣ ‹‹አሜሪካና 16ቱ የስለላ ተቋሞቿ›› እና ‹‹የአበው አንደበት›› የተሰኙ መፅሀፍትን ለንባብ ያበቁ ሲሆን በቀጣይም “ጓዜና ጉዞዬ”፣ “የምርመራ ጥበቦች” እና ‹‹ያልተነበበው መፅሀፍ›› 1 እና 2ን ለንባብ ለማብቃት መዘጋጀታቸውን ገልፀዋል፡፡

ሞባይል ስልክ ለ3.8 ሚ. አፍሪካውያን የስራ ዕድል ፈጥሯል
     በአፍሪካ የሞባይል ስልክ ተጠቃሚዎች ቁጥር 557 ሚሊዮን መድረሱንና  የአህጉሪቱ ኢኮኖሚ ባለፈው የፈረንጆች አመት 2015 ከሞባይል ምርትና አገልግሎት 153 ቢሊዮን ዶላር ማግኘቱን ፎርብስ መጽሄት ዘገበ፡፡
የአፍሪካ የሞባይል ኢኮኖሚ የ2016 ሪፖርትን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ከአህጉሪቱ አጠቃላይ የሞባይል ተጠቃሚዎች ቁጥር ከ30 በመቶ በላይ የሚሆነውን የሚሸፍኑት የግብጽ፣ የናይጀሪያና የደቡብ አፍሪካ ተጠቃሚዎች ሲሆኑ፣ የሞባይል ስልክ ኢንዱስትሪው በ2015 ብቻ ለ3.8 ሚሊዮን አፍሪካውያን  የስራ ዕድል ፈጥሯል፡፡
በመጪዎቹ አምስት አመታት በአፍሪካ ተጨማሪ 168 ሚሊዮን ሰዎች የሞባይል አገልግሎት ተጠቃሚዎች እንደሚሆኑና ይህም የተጠቃሚዎችን ቁጥር 725 ሚሊዮን ያደርሰዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ዘገባው፤ በአህጉሪቱ አገልግሎት የሚሰጡ የስማርት ሞባይል ስልኮች ቁጥር በሶስት እጥፍ ያድጋል ተብሎ እንደሚገመትም ገልጧል፡፡ በእነዚህ አምስት አመታት የሞባይል ተጠቃሚዎች ይሆናሉ ተብለው ከሚጠበቁ 168 ሚሊዮን አፍሪካውያን መካከልም ከ30 በመቶ በላይ  ኢትዮጵያውያን፣ ናይጀሪያውያንና ታንዛኒያውያን እንደሚሆኑም ተገልጧል፡፡
በሞባይል ስልክ አማካይነት የኢንተርኔት አገልግሎት የሚያገኙ አፍሪካውያን ቁጥርም፣ ባለፉት ሶስት አመታት በሶስት እጥፍ በማደግ፣ በ2015 የፈረንጆች አመት 300 ሚሊዮን መድረሱን የጠቆመው ዘገባው፤ የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ቁጥር በመጪዎቹ አምስት አመታት 550 ሚሊዮን ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅም አስረድቷል፡፡

      በጁባ ባለፉት 3 ሳምንታት ብቻ ከ120 በላይ ጾታዊ ጥቃቶች ተፈጽመዋል
      የደቡብ ሱዳኑ ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር ምክትላቸው የነበሩትን ተቀናቃኛቸውን ሬክ ማቻርን ከስልጣን አውርደው ጄኔራል ታባል ዴንግ ጋይን በቦታው መተካታቸውን ተከትሎ፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በአገሪቱ የሚደረጉ የስልጣን ሹም ሽሮች በሙሉ የሰላም ስምምነቱን ያከበሩ መሆን አለባቸው በሚል ፕሬዚደንት ሳልቫ ኬርን ማስጠንቀቁን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር ሹም ሽሩን ማድረጋቸው በሁለቱ የአገሪቱ ተቀናቃኝ ሃይሎች መካከል ከስምንት ወራት በፊት የተደረገውን የሰላም ስምምነት የሚጥስና አገሪቱን ወደከፋ ጦርነት ሊያመራ የሚችል ነው መባሉን የጠቆመው ዘገባው፣ በሳልቫ ኬርና በማቻር መካከል በዚህ ወር ዳግም ግጭት መቀስቀሱን ጠቅሷል፡፡
ግጭቱ መቀስቀሱን ተከትሎ ማቻር ወታደሮቻቸውን ይዘው ከመዲናዋ መውጣታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ሳልቫ ኬርም ባለፈው ሳምንት ባወጡት መግለጫ ማቻር በአፋጣኝ ወደ ጁባ ካልተመለሱ ከስልጣናቸው እንደሚነሱ ማስታወቃቸውን ገልጧል፡፡ በሁለቱ ተቀናቃኝ ሃይሎች መካከል የተደረሰው የሰላም ስምምነት፣ የአገሪቱ ምክትል ፕሬዚዳንት በተቃዋሚው ሃይል ይመረጣል የሚል አንቀጽ ማካተቱን ያስታወሰው ዘገባው፣ ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር አዲሱን ምክትል ፕሬዚደንት መሾማቸው ከስምምነቱ ጋር የማይጣጣም እንደሆነም አስታውቋል፡፡
ሮይተርስ በበኩሉ፤ በአገሪቱ መዲና ጁባ ባለፉት ሶስት ሳምንታት ብቻ ከ120 በላይ የጾታዊ ጥቃትና የአስገድዶ መድፈር ድርጊቶች ተፈጽመዋል ሲል ተመድ ባለፈው ረቡዕ ማስታወቁን ዘግቧል፡፡ የተመድ ቃል አቀባይ ፋራህ ሃቃን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፤ወታደሮችና ሲቪል የለበሱ ግለሰቦች ግጭቱን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም፣ በሴቶችና በህጻናት ላይ አሰቃቂ የጾታ ጥቃቶችን ፈጽመዋል፡፡

Saturday, 30 July 2016 11:54

ዕዳ ከሜዳ

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አዝማሪ ጠዋት ማለዳ ተነስቶ ለሚስቱ፡-
“ዛሬ ከቤት ውጣ ውጣ ብሎኛል” ይላታል፡፡
ሚስቲቱም፤
“ወዴት ነው ውጣ ውጣ ያለህ?” ስትል ትጠይቀዋለች፡፡
“ወደ ሆነ ጫካ ሄጄ መዝፈን ፈልጌያለሁ”
ሚስቲቱም፤
“እኔ አልታየኝም፡፡ ደግሞስ ከመቼ ወዲያ ያመጣኸው ፀባይ ነው? እኔ ቀፎኛል፡፡ መዝፈንም ከሆነ ያማረህ እዚሁ ቁጭ ብለህ እንደልብህ እየጮህክ ዝፈን ምን ጫካ ለጫካ ያንከራትትሃል?” አዝማሪውም፤
“በገዛ አገሬ ጫካ ብሄድ፣ ሜዳውን ብጋልብ፣ ያሰኘኝን ባረግ ምን እንዳልሆን ብለሽ? እባክሽ ፍቀጂልኝና ዱር ሄጄ ዘፍኜ ይውጣልኝ” ሲል ለመናት፡፡
“እንግዲህ ይሄን ያህል ተንገብግቤለታለሁ ብለህ ልብህ ከተነሳ እዚህ ቁጭ ብለህም ምንም አትፈይድልኝ፤ ይሁን ሂድና ያሰብከው ይሙላልህ” አለችው፡፡
አዝማሪው ደስ ብሎት ወደ ዱር ሄዶ አንድ ትልቅ የዋርካ ዛፍ ስር ተቀምጦ ክራሩን ቃኝቶ፤ በሚያምር ድምፅ፤ ጮክ ብሎ፣ መዝፈን ይጀምራል፡፡
“ኧረ ፋኖ ፋኖ፣ አንት አሞተ መረራ የልብህ ሳይሞላ፣ ተኝተህ አትደር፡፡
ሜዳላይ አይድከም፣ ለዳገት የጫንከው የልቡን አርጎ ነው፤ ጀግና እፎይ የሚለው፡፡”
ይህን እየዘፈነ ፍንድቅድቅ እያለ አርፍዶ በድንገት ወደሱ የሚመጣ የእግር ኮቴ ሰማ፡፡ በርካታ ሰዎች መጥተው ከበቡት፡፡
እነዚህ ሰዎች በሬያቸው ተሰርቆባቸው ፍለጋ ላይ ናቸው፡፡
“የበሬያችን ሌባ ተገኘ፡፡ ያዙት! ያዙት!” እያሉ ይቀጠቅጡት ጀመር፡፡
አዝማሪው
“እረ ጌቶች፤ እኔ በሬ እሚባል አላየሁም፡፡”
“አንተ ነህ እንጂ የሰረቅኸው! ይሄው ከጀርባህ ያለውን አታይም፡፡ ሥጋውን በልተህ በልተህ ስትጠግብ የተረፈህን ሰቅለህ፤ በጥጋብ ትዘፍናለህ፡፡ ቆዳውም ያው የኛ በሬ መልክ ነው ያለው፡፡ መስረቅህ አንሶ ልታታልለን ትፈልጋለህ?” እያሉ እንዳይሞት እንዳይድን አድርገው ቀጥቅጠው፣ እጅ እግሩን አስረው፤ ጥለውት ሄዱ፡፡ የተረፈውን ስጋ ይዘው ሄዱ፡፡ ሚስቱ ወደ አመሻሹ ላይ ቤት ሳይመለስ በመቅረቱ ሰው ይዛ በጫካው ስታስፈልገው ዋርካው ስር ተኮራምቶ ተኝቶ ተገኘ፡፡
“ምነው ምን ሆንክ?” ብትለው፤
“እረ ተይኝ፡፡ ዕዳ ከሜዳ ነው የገጠመኝ!”
*   *   *
በል በል አለኝ፣ እንዲህ አርግ አሰኘኝ ብለን በዘፈቀደ የምናደርገው ነገር ዕዳ ከሜዳ ያመጣል፡፡ አካባቢን፣ ግራ ቀኙን በቅጡ አለማየትና አለመመርር ዕዳ ከሜዳ ያመጣል። የሌሎች ግንዛቤና የእኛ ግንዛቤ ላይጣጣም ይችላልና የሀሳብ ርቀትን ልብ እንበል። ደምቦች፣ መመሪያዎች፣ አዋጆች የድንገቴ ሲሆኑ ህዝብ ላይ ዕዳ ከሜዳ ይሆናሉ፡፡ ዕዳ ከሜዳ መሆናቸው ሳያንስ የአፈፃፀም ችግር ካለ ደግሞ ይብሱን ከድጡ ወደማጡ ይሆናል፡፡
ስለአፈፃፀም ችግር ሌት-ተቀን ቢወተወትም ‹‹ወይ›› ያለ የሥራ ኃላፊ፣ ‹‹እሺ እናርማን› የሚል፣ ጉዳዩ የሚመለከተው ባለሥልጣን ወይም አለቃ አልተገኘም፡፡ ችግሮች የማያባራ ዝናብ የሆኑ አንድም በምንግዴ ነው፤ አንድም ሠንሠለታዊ ባህሪ ስላላቸው ማን ማንን ይነካል ነው፤ አሊያም እከክልኝ ልከክልህ ነው፤ ወይም ደግሞ የአቅም ማነስ ነው፡፡ የችግሮች ባለቤት ማጣትም ሌላው ችግር ነው፡፡ የአንድ ሰሞን ሆይ ሆይታም ዓይነተኛ አባዜችን ነው፡፡ አንድ ነገር የተሸከመው ችግር ሳያንስ፤ ቆሻሻ ማንሳት ችግር ሆኖ ሲያነጋግር ማየትና መስማት እጅግ አሳፋሪ ነው፡፡ ዛሬ እንደ ዘበት ‹‹ቆሻሻ ውስጤ ነው!›› እየተባለ ሲቀለድ መስማት ይዘገንናል፡፡ ስለለውጥ ማውራት ከጀመርን ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ዛሬም ውሃ የለም፡፡ ሆኖም ስለአተት እናትታለን። ዛሬም መብራት የለም፡፡ አገር እየተሰጠነች ስትሄድ መብራት የኃይል ምንጭነቱ የህልውና ጉዳይ ይሆናል እንጂ ዛራና ቻንድራን ለመመልከቻ አሊያም ስፖርት መከታተያ አይደለም ዋናው ጭንቅ ስለምጣድና የእለት እንጀራ ማሰብ ግዴታ ነው። ስለኢንዱስትሪ መፈጠር ነጋ-ጠባ የምንወተውተው ካለኤሌትሪክ ግባት ከሆነ የታሪክ ምፀት ይሆናል! የትራንስፖት እጥረት፣ ያውም በክረምት፣ እሰቃቂ ሆኗል፡፡ ከጫፍ እስከጫፍ አንዳንዴም ሰልፍ ዞሮ የት ገባ እስከሚባል ድረስ እየተምዘገዘገ የሚሄደው ሰልፍ ከዕለት ዕለት እየረዘመ መምጣቱን ለማንም አለቃ መነገር ያለበት ጉዳይ አልሆነም፡፡ ፀሀይ የሞቀው ጉዳዳ ነውና፡፡ ይልቁንም ህዝብ ትዕግሥቱንና ልቦናውን ሰጥቶት በሥነ-ስርዓት ሰልፍ ገብቶ ራሱን ማስተናገዱና ቅጥ ስለ መፍጠሩ ሊመሰገን ይገባል ያም ሆኖ በየተቋማቱ ዘንድ አሁንም የአፈፃፀም ችግር የማይዘለል ችግር ነውና። የዘፈቀደ አሰራር ሥር ከሰደደ አድሮ ዕዳ ከሜዳ መሆኑ አይቀሬ ነው! ግምገማ ውሃ ወቀጣ እንዳይሆን እናስብበት!

    ስምንት የምስራቃዊ አውሮፓ አገራት ባለፉት አራት አመታት ብቻ ከ1 ቢሊዮን ፓውንድ በላይ የሚያወጣ የጦር መሳሪያ ለመካከለኛው ምስራቅ አገራት መሸጣቸው በምርመራ መረጋገጡን ዘ ጋርዲያን ዘገበ፡፡
ባልካን ኢንቬስቲጌቲቭ ሪፖርቲንግ ኔትዎርክና ኦርጋናይዝድ ክራይም ኤንድ ኮራፕሽን ሪፖርቲንግ ፕሮጀክት የተባሉ ተቋማት ያወጡትን መረጃ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፤ ከ8 የምስራቃዊ አውሮፓ አገራት ወደ መካከለኛው ምስራቅ አገራት ከገቡት በሺህዎች የሚቆጠሩ የተለያዩ ከባድና ቀላል የጦር መሳሪያዎች መካከል አብዛኞቹ በእርስ በርስ ጦርነት ወደምትታመሰው ሶርያ ደርሰው ጥቅም ላይ እየዋሉ ይገኛሉ፡፡  የጦር መሳሪያዎቹን የሸጡት አገራት ቦስኒያ፣ ቡልጋሪያ፣ ክሮሺያ፣ ቼክ ሪፐብሊክ፣ ሞንቴኔግሮ፣ ስሎቫኪያ፣ ሰርቢያና ሮማኒያ እንደሆኑ ለአንድ አመት በዘለቀ የተደራጀ ምርመራ መረጋገጡን የጠቆመው ዘገባው፤ አገራቱ እ.ኤ.አ ከ2012 አንስቶ ባሉት አመታት በድምሩ 1 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጣ የጦር መሳሪያ ለሳኡዲ አረቢያ፣ ለዮርዳኖስ፣ ለተባበሩት አረብ ኢሜሬትስና ለቱርክ ሸጠዋል ብሏል፡፡ የጦር መሳሪያዎቹ በመካከለኛው ምስራቅ አገራት በሚገኙ አክራሪ ቡድኖች በጥቅም ላይ እየዋሉ እንደሚገኙ መነገሩን የጠቆመው ዘገባው፤ አምነስቲ ኢንተርናሽናልና የአውሮፓ ህብረት ከሽያጩ ጋር በተያያዘ ተቃውሟቸውን ማሰማታቸውንና የህብረቱ ፓርላማ ከፍተኛ ባለስልጣንም አንዳንዶቹ ሽያጮች የአውሮፓ ህብረትን የጦር መሳሪያ ሽያጭ ብሄራዊና አለማቀፍ ህጎች የሚጥሱ ናቸው ማለታቸውን አመልክቷል፡፡ 

“በወረዳ አመራሮች የሚሰሩ ስህተቶች መንግስትን ከፍተኛ ዋጋ እያስከፈለው ነው”

   መንግስት ‹‹ህገ ወጥ›› ያላቸውን ቤቶች ያፈረሠበት መንገድ በአለማቀፍ የሠብአዊ መብቶች ድንጋጌና በህግ ተቀባይነት እንደሌለው የገለጹ የህግ ባለሙያዎች፤ድርጊቱ የህግ ተጠያቂነትን ሊያስከትል እንደሚችል ተናገሩ፡፡ ቤታቸው ለፈረሰባቸው ዜጎች፣መንግስት ተለዋጭ ቤት መስጠት አለበትም ብለዋል - የህግ ባለሙያዎቹ፡፡  
ዓለማቀፍ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች ስምምነት፤ማንኛውም ሰው ደህንነቱ እንዲጠበቅና መኖሪያ ቤቱ እንዲከበር በፅኑ ይደነግጋል ያሉት አለማቀፍ የህግ ባለሙያው ዶ/ር ያዕቆብ ወ/ማርያም፤በተለያዩ የሠብዓዊ መብት ስምምነቶች፣ የመኖሪያ ቤት ጉዳይ በዋናነት ጥበቃ የሚደረግለት መሆኑን ይገልጻሉ፡፡   
‹‹ሠዎች ህገ-ወጥ ቤት ቢሠሩ እንኳን ቤቶቹ ሲሠሩ በዝምታ የታለፉ እንደመሆናቸው በድጋሚ አይፈርሱም›› ያሉት ዶ/ር ያዕቆብ፤ ‹‹በተለያዩ ሃገራት በህገ ወጥ መንገድ ቤት የሠሩ ሰዎች ካሳ ከፍለው ቤቱ ህጋዊ ይሆንላቸዋል” ሲሉ የሌሎች አገራትን ተመክሮ ጠቅሰዋል፡፡ በቅርቡ የአዲስ አበባ አስተዳደር ያፈረሳቸው ቤቶች አፈራረስም የኢትዮጵያንም ሆነ ዓለማቀፍ የሠብዓዊ መብት ድንጋጌዎችን የጣሰና ዜጎችን ያለ አግባብ ለእንግልት የዳረገ ነው የሚሉት የህግ ባለሙያው፤ ‹‹የከተማ አስተዳደሩ የግድ ማፍረስ አለብኝ ካለም በቅድሚያ ቤት ሊያዘጋጅላቸው ወይም ቤት ሊያሰራቸው የሚችል ተመጣጣኝ ካሣ መክፈል ነበረበት፤ይህን አለማድረጉ በሠብአዊ መብት ጥሰት ሊያስጠይቀው ይችላል›› ብለዋል፡፡
“አስተዳደሩ ቤቶቹ ሲሠሩ እያየ ዝም ካለ፣የቤቶቹን መሰራት እንደፈቀደ ይቆጠራል” ያሉት የህግ ባለሙያው፤ነዋሪዎች መብራትና ውሃ የመሳሰሉ መሠረተ ልማቶችን ሲያሟሉ በዝምታ ማለፉ ብቻውን ቤቶቹን ህጋዊ ያደርጋቸዋል ሲሉም ይሞግታሉ፡፡ ቤቶቹ መፍረስ አይገባቸውም ነበር፤ ስለዚህ አስተዳደሩ የፈፀመው ህገ-ወጥ ድርጊት ነው” ብለዋል፡፡
ይህን የአስተዳደሩን ድርጊት ማረም የሚቻለው መንግስት ለተጎጂዎቹ በቂ ካሳ ሲከፍልና ቤት ሰርቶ ሲሰጣቸው ብቻ ነው ያሉት ዶ/ር ያዕቆብ፤‹‹ወቅቱን ባላገናዘበ መልኩ ቤቶችን በጅምላ አፍርሶ ዜጎችን ሜዳ ላይ መጣል አለማቀፍ የሠብአዊ መብት ድንጋጌዎችን ፈፅሞ የተቃረነ ኢ-ሠብአዊ ድርጊት ነው” ብለዋል፡፡ ቤቶቹን በማፍረስ ተግባር ላይ የተሣተፉ ግለሰቦችም ሆኑ ባለስልጣናትም በግላቸው በህግ መጠየቅ እንዳለባቸው ዶ/ር ያዕቆብ ይናገራሉ፡፡
የህግ መምህርና ባለሙያ አቶ ቁምላቸው ዳኜ በበኩላቸው፤የመጠለያ ጉዳይ በአለማቀፍ የሠብአዊ መብት ድንጋጌዎች ውስጥ በህይወት ከመኖር መብት ጋር ተያይዞ የሚታይ መሆኑን ጠቅሰው፣መጠለያን በዚህ መልኩ ማሳጣት የሠብዓዊ መብት ክብርን የመግፈፍ ድርጊት ነው ብለዋል፡፡ አለማቀፉ የሠብአዊ መብት ድንጋጌ፣ የመንግስት በሲቪል መብቶች ላይ ጣልቃ መግባትን እንደሚከለክል የጠቀሱት ባለሙያው፤መንግስት ቤቶቹን ያፈረሠበት መንገድም በዚህ የህግ ጥሰት የሚታይ ነው ሲሉ አሰረድተዋል፡፡
መንግስት ለዜጎች መጠለያ ማቅረብ ካልቻለ ለራሳቸው እንዲሰሩ ሁኔታዎችን ማመቻቸት እንዳለበት የጠቀሱት የህግ ባለሙያው፤ለዚህ አንደኛው መፍትሄ ቤቶቹን ከማፍረስ ይልቅ ወደ ህጋዊ መስመር የሚገቡበትን መንገድ ማመቻቸት ነበር ብለዋል፡፡ ቤቶቹ ሲገነቡ መጀመሪያ ማስቆም ይገባ ነበር ያሉት የህግ ባለሙያው፤ቤቶቹ ከተገነቡ በኋላና ዜጎች በተለያየ መንገድ ህጋዊነት እንዲሰማቸው ከተደረገ በኋላ ማፍረሱ የሠብአዊ መብት ጥሰት ነው ብለዋል፡፡
ግለሰቦቹ መብራት ያስገቡበት፣ ሌሎች የልማት መዋጮዎችን ያወራረዱበት ሰነድ ካላቸውና ወረዳው እያወቀ መሰረተ ልማቶችን ያሟሉ ከሆነ፣ በከፊል ህጋዊ እንደሆኑ ይቆጠራል ያሉት ሌላው ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የህግ ባለሙያ፤ መንግስት ከዚህ አንፃር መሰረታዊ ስህተቶች መሰራታቸውን አምኖ፣ለተጎጂዎች ተገቢውን ካሳና መጠለያ ሊያቀርብ ይገባል ብለዋል፡፡
ግለሰቦቹ ህገወጥ ናቸው ከተባሉም ግልፅ አማራጮች ተቀምጠው፣በቀጥታ የሚያርፉበት ምትክ መጠለያ ተዘጋጅቶላቸው፣ፍትሃዊ በሆነ ሂደት ተዳኝተው፣ የፍ/ቤት ትዕዛዝ ሲገኝ ብቻ ነው ቤቶች ሊፈርሱ የሚገባው ሲሉ ባለሙያው አስረድተዋል፡፡ “በቂ ማስጠንቀቂያ ሳይሰጠን ነው ቤታችን እንዲፈርስ የተደረገው” የሚለው የዜጎች አቤቱታም ከህግ አንፃር መንግስትን ሊያስጠይቀው ይችላል ብለዋል፤የህግ ባለሙያው፡፡
 የምጣኔ ሀብት ባለሙያው ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ በርሄ በበኩላቸው፤መንግስት ቤቶቹን ከማፍረሱ በፊት ደጋግሞ ማሰብና የተለያዩ አማራጮችን ማስቀመጥ ይገባው ነበር ይላሉ፡፡ ህዝቡ መኖሪያ ቤት የሚያገኝበትን መንገድ መንግስት በሚገባ ማሰብ አለበት የሚሉት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤ “ሰዎቹ ከገበሬ ላይ ቦታ ገዝተው ቤት ሰርተው የሚኖሩ ከሆነ፣መጠነኛም ቢሆን ገንዘብ ያላቸው መሆኑን የሚያመለክት በመሆኑ፣መንግስት ራሱ ዲዛይን አውጥቶላቸው በህጋዊ መንገድ በማህበር ተደራጅተው ኮንዶሚኒየም እንዲሰሩ ቢያደርግ ለችግሩ መፍትሄ ይሆናል” ብለዋል፡፡  
“ፈረሱ የተባሉት ቤቶች መሰረተ ልማት እስኪሟላላቸው ድረስ ወረዳና ክ/ከተማ ያሉ የመንግስት አካላት የት ነበሩ?” ሲሉ የሚጠይቁት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤“በወረዳና ክፍለ ከተማ አመራሮች የሚሰሩ ስህተቶች መንግስትን በከፍተኛ መጠን ዋጋ እያስከፈለው ነው” ብለዋል፡፡
መንግስት በወረዳ ደረጃ በአመራርነት መመደብ ያለበት ብቃት ያላቸውን ሰዎች ሊሆን ይገባል የሚሉት የምጣኔ ሃብት ባለሙያው፤እነዚህ የፈረሱ ቤቶች ይሄን ያህል አመት የቆዩት በተለያየ መንገድ የወረዳ አመራሮች ቢፈቅዱላቸው ነው፤በቤቶቹ ግንባታ ላይ የወረዳ አመራሮች እጅ አለበት ብለዋል፡፡ ቤቶቹ ከመፍረሳቸው በፊት ሌሎች አማራጮች በስፋት ሊታዩ ይገባ ነበር ያሉት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤በቀጣይም ቤታቸው የፈረሰባቸው ዜጎች ቤት ማግኘት መቻል አለባቸው፤መንግስትም መፍትሄ ያገኝለታል የሚል እምነት አለኝ ብለዋል፡፡



     የደንበኞች ቀንን ለ3ኛ ጊዜ ያከበረው መሰቦ ሲሚንቶ ፋብሪካ፤የገበያ ድርሻዬን አሳድገውልኛል ፣አጋርም ሆነውኛል ያላቸውን ደንበኞቹን ባለፈው ቅዳሜ ሐምሌ 16 ቀን፣ በባህር ዳር ከተማ ሸለመ፡፡
የሲሚንቶ ምርቶቹን በማጓጓዝና ምርቶቹን በመጠቀም ሁነኛ ደንበኞቼ ናቸው ያላቸውን በርካታ ድርጅቶች ፋብሪካው በተለያዩ ደረጃዎች የሸለመ ሲሆን በትራንስፖርት ዘርፍ የላቀ ተሸላሚ በመሆን ትራንስ ኢትዮጵያ ተጠቃሽ ነው፡፡ ምርቶቹን በማስፋፋት ደግሞ ጉና ትሬዲንግ ተሸልሟል፡፡ ምርቶቹን በመጠቀም የላቀ ሽልማት ከተሰጣቸው መካከል የአዲስ አበባ ቤቶች ግንባታ ፅ/ቤትና የህዳሴውን ግድብ የሚገነባው ሳሊኒ ኮንስትራክሽን በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳሉ፡፡  
የፋብሪካው ስራ አስኪያጅ አቶ ክብረአብ ተወልደ፤ፋብሪካው ዋነኛ ችግሩ ምርቶቹን በራሱ ትራንስፖርት ማጓጓዝ አለመቻሉ መሆኑን ጠቅሰው፣ በቀጣይ በራሱ ትራንስፖርት ለማጓጓዝ  200 ተሽከርካሪዎችን በ877 ሚሊዬን ብር መግዛቱን ተናግረዋል፡፡ እስካሁን ፋብሪካው ምርቶቹን የሚያሰራጨው ከግል ትራንስፖርት ሰጪዎች ጋር ውለታ በመግባት እንደነበርም ሥራ አስኪያጁ አውስተዋል፡፡  
መሰቦ ሲሚንቶ፤ ግልገል ጊቤ 1, 2 እና 3 እንዲሁም ታላቁ ህዳሴ ግድብን ጨምሮ ለመንግስት የተለያዩ ቤቶች ግንባታ ፕሮጀክቶች ምርቶቹን እያቀረበ ሲሆን በሀገሪቱ የገበያ ድርሻውም ወደ 24 በመቶ ከፍ ማለቱን ስራ አስኪያጁ ተናግረዋል፡፡ ፋብሪካው በዓመት 2.3 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ሲሚንቶ የማምረት አቅም ያለው ሲሆን በየጊዜው አቅሙን የሚያሳድጉ የማስፋፊያ ስራዎችንም እየሰራ ነው ተብሏል፡፡