Administrator

Administrator

Saturday, 03 August 2013 11:03

“…የወንዶች መካንነት…”

ቀደም ያሉ ጥናቶች እንደሚያሳዩት ለዘር መካንነት የሚበቁ ወንዶች ችግር ከአእምሮ ጋር የተገናኘ መሆኑን የሚያመላክት ሲሆን በቅርብ የወጡት ደግሞ 90% የሚሆኑት ምክንያቶች የተፈጥሮ ወይንም አካላዊ ችግሮች መሆናቸውን ይገልጻሉ ፡፡ ቢሆንም ግን ከአካላዊ ችግር የተነሳ መውለድ ያቃታቸውም ቢሆኑ ሁኔታው በመከሰቱ እራሳቸውን ዝቅ አድርገው መመልከት፣ መበሳጨት፣ እራስን እንደጥፋተኛ የመቁጠር ሁኔታዎች ስለሚታይባቸው የአእምሮ ወይንም የአስተሳሰብ ችግርም ይገጥማቸዋል፡፡ ወንዶች ለመካንነት ያላቸው ድርሻ ምን ያህል ነው? የሚለውን በዚህ እትም ለንባብ ያልን ሲሆን ማብራሪያውን የሚሰጡት ዶ/ር እስክንድር ከበደ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ትምህርት ቤትጥቁር አንበሳ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስትና መምህር ናቸው።
ጥ/ መካንነት እንዴት ይገለጻል?
መ/ መካንነት ማለት ጥንዶች ለአንድ አመት ያህል አብረው እየኖሩ ነገር ግን ሴቲቱ ልጅ ማርገዝ ካልቻለች የመካንት ችግር አለ ብሎ መደምደም ይቻላል፡፡ ይህ አገላለጽ የሚጠቅመው ጥንዶች አብረው እየኖሩ ልጅ መውለድ አልቻልንም ብለው ምክንያቱን ሊያስቡና ወደሕክምና ሄደውም መፍትሄውን መጠየቅ የሚችሉበትን ጊዜ ለመጠቆም እንዲረዳ ነው፡፡ በእርግጥ ይህንን ጊዜ በእድሜ ልዩነት ከፋፍሎ መመልከት ያስፈልጋል፡፡ ተጋቢዎቹ ወጣት ከሆኑ እስከ አንድ አመት ሁኔታውን በትእግስት መከታተል ሲገባ ነገር ግን ሴቲቱ ከ35/አመት በላይ ከሆነች እስከአንድ አመትም መታገስ ሳያስፈልግ ቀደም ብሎ መከታተል ይገባል፡፡
ጥ/ ለመካንነት የወንዶች ድርሻ ምን ያህል ነው?
መ/ ቀደም ባሉት ጊዜያት ጥንዶች ልጅ መውለድ ካልቻሉ መካን የሆነችው ሴትዋ ነች እንጂ የወንድ መካን የለም ብለው ያምኑ ነበር፡፡ ይህ ግን የተሳሳተ አመለካከት ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ በአለው የሳይንስ እድገት እንደተረጋገጠው ከሆነ በጥንዶች መካከል ለመካንነት የወንዶች ተሰትፎ ወደ 20% ይሆናል፡፡ በእርግጥ በሴትዋም በወንዱም በኩል ልጅ ያለማግኘት ችግር ሲከሰት ለምክንያትነቱ ከ20-40% ያህል ወንዶች ናቸው።
ጥ/ ለወንዶች መካንነት ምክንያቱ ምንድነው?
መ/ ወንዶች መካን ሆኑ ሲባል በአራት ሊከፈል ይችላል፡፡
በጭንቅላት አካባቢ የሚፈጠሩ ችግሮች (1-2%)
ፒቱታሪ ግላንድ ላይ ስራቸውን የሚሰሩ ሆርሞኖች ማነስ ፣የፒቱታሪ ግላንድ እጢዎች መኖር ፣በተለያዩ ሕመሞች ምክንያት የሚወሰዱ አንዳንድ መድሀኒቶች ፣በተለያዩ ምክንያቶች በጭንቅላት ላይ የሚደርሱ አደጋዎች፣ እንደ ቲቢ ፣የስኩዋር በሽታ ያሉ አድካሚ በሽታዎች ፣መነንጃይትስ የመሳሰሉ ለኢንፌክሽን የሚያጋልጡ ሕመሞች፣ ከመጠን በላይ ውፍረት መካንነትን በወንዶች ላይ ሊያስከትል ይችላል፡፡
በዘር ፍሬ ማምረቻ Testis ላይ የሚፈጠር ችግር (30-40%)
የዘር ማመንጫ ወይንም ማስቋሽቋ የሚ ባለው የሰውነት ክፍል በትክክለኛው አፈጣጠር 46/ ክሮሞዞም ሊኖረው ሲገባ ነገር ግን አንድ ተጨማሪ ማለትም 47/ክሮሞዞም ቢኖራቸው ሙሉ በሙሉ መካን ያደርጋል፡፡
ወንድ ሲፈጠር የዘር ማመንጫው የሚገኘው በሆድ ውስጥ ነው፡፡ ነገር ግን ቀስ በቀስ ወደ ትክክለኛው ቦታው የሚመጣ ይሆናል፡፡ ልጁ ከተወለደ ከአንድ አመት በላይ የዘር ማመንጫው በተፈጠረበት ሆድ እቃ ውስጥ ከቆየ የመካንነት ችግር ሊያጋጥም ይችላልዶ/ር እስክንድር ከበደ ከመካንነት ባለፈም የካንሰር ችግርም ሊያጋጥም ይችላል፡፡ ስለዚህም በጊዜው በኦፕራ ሲዮን መስተካከል ይገባዋል፡፡
የደም መልስ ቡዋንቡዋዎች መስፋት የወንድ ዘርፍሬ ማመንጫ አካባቢ ሙቀት በመፍጠር ትክክለኛ የሆነ የስፐርም አፈጣጠር ሂደት እንዳይኖር ያደርጋል። ጆሮ ደግፍ የሚባል በሽታ ወንዶ በእድሜያቸው ከጉርምስና በሁዋላ ሲደርሱ ከታመሙ ወደ 25% የሚሆኑት የዘር ማመንጫ ፍሬውን ስለሚጎዱ መካንነትን ሊያስከትል ይችላል፡፡ በአብዛኛው ግን ጆሮ ደግፍ በሽታ በልጅነት ስለሚይዝ ለዚህ ችግር ብዙዎችን አይዳርግም፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የስጋ ደዌ በሽታ በልጅነት እድሜ ከያዘ እንዲሁም ቲቢ የተባለው በሽታ በጊዜው ካልታከመ ለወንዶች የመካንነት ችግርን ሊያስከትል ይችላል፡፡ ለካንሰር የሚወሰዱ መድሀኒቶች፣ የጨረር ሕክምና በዘር ፍሬ ማምረቻው ከተወሰነ መጠን በላይ ካረፈ የዘር ፍሬውን ስለሚያበላሽ መካን ያደርጋል፡፡ የኩላሊት ወይንም የጉበት በሽታ እንዲሁም ካንሰር ከመጨረሻው ደረጃ ላይ ከደረሱ የወንድ የዘር ፍሬ ውጤታማ እንዳይሆን ስለሚያደርጉ መካንትን ያስከትላሉ፡፡
ስፐርም ከተመረተ በሁዋላ ወደውጭ እንዲፈስ ባለው አካሄድ መስመሩ ወይንም
መጉዋጉዋዣው ሲዘጋ (20-30%)
እስፐርም ከተመረተ በሁዋላ ወደሴቷ እንቁላል በመጉዋዝ ልጅ እንዲመረት የሚያደ ርገው መስመር በተለምዶው የትራንስፖርት መስመር ይባላል። ይህ መስመር ማለትም የዘር ማስተላለፊያው ቱቦ በኢንፌክሽን ወይንም ቀደም ብሎ ባጋጠመ እንደ ጨብጥ ባሉ በተለያዩ በሽታዎች ምክንያት መስመሩ ከተዘጋ አለዚያም በተፈጥሮ ምክንያት ቱቦው እስከጭርሱንም ላይፈጠር ስለሚችል እንደ አንድ ችግር ሊቆጠር የሚችል ነው፡፡
ምክንያቱ የማይታወቅ (ከ40-50%)
በተለያዩ የአኑዋኑዋር ሁኔታዎች ማለትም ሲጋራ ማጨስ፣ የአደንዛዥ እጾችን መውሰድ፣ አልኮሆል በከፍተኛ ሁኔታ መውሰድ፣ ከባድና ተከታታይ የሆነ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ማድረግ፣ በጣም ጠባብ የሆነ የውስጥ ሱሪ መልበስ፣ የአካባቢ አየርን መበከል ለሚችሉ መርዛማ ኬሚካሎች መጋለጥ፣ የተመጣጠነ ምግብ እጥረት፣ ከፍተኛ ጭንቀት ...ወዘተ አንድን ወንድ ለመካንነት ሊዳርጉ ከሚችሉ መካከል ናቸው፡፡
ጥ/ ሕክምና አለው?
መ/ ሕክምና አለው፡፡ ሕክምና ሲባል ግን መጀመሪያ ጥንዶቹ መካንነትን ለማረጋገጥ በጋራ
ከሐኪሙ ጋ ሲቀርቡ የሚጀመር ነው፡፡ ብዙውን ጊዜ ጥንዶች ልጅ ማግኘት ካልቻሉ ተፈጥሮአዊውም ይሁን ሰው ሰራሹ ችግሩ ከሴትዋ ይሆናል የሚል ግምት በመያዝ ወንዶቹ ሐኪም ጋ አይቀርቡም፡፡ ሴቶቹ ብቻ ምርመራ በማድረጋቸው የሚገኘው ውጤት አመርቂ አይሆንም፡፡ ስለሆነም ጥንዶች በጋር ምርመራ ሲጀምሩ መጀመሪያ ዝርዝር የሆነውን ታሪካቸውን በመውሰድ በተለይም ወንዶቹን በሚመለከት፡-
የዘርፍሬው አፈጣጠር እና ያሉበት ቦታ ትክክለኛ ነው አይደለም ?
ቫሪኮስ የሚባለው ማለትም የደም ስሮቹ የመስፋት ሁኔታ ይታይባቸዋል ወይ?
ቱቦው በትክክል ተፈጥሮአል ወይ?
ሰውየው ትክክለኛ የሆነ ወሲባዊ እንቅስቃሴ አለው የለውም? ...ወዘተ
ከላይ የተመለከቱት ጥያቄዎች ባካተተ ሁኔታ በምርመራ ከተረጋገጠ በሁዋላ ፈሳሹ ተወስዶ ምርመራው ይቀጥላል፡፡ በዚህም ከወንዱ የሚወጣው ዘር መጠን ትክክለኛነት እንዲሁም አሲድ አለው የለውም? ቅጥነቱ ፣ውፍረቱ ፣የስፐርም ቁጥሩ እንዲሁም በአንድ ጊዜ በሚወጣው ፈሳሽ ውስጥ ምን ያህል ስፐርም አለ? እንቅስቃሴያቸውና አፈጣጠራቸው ትክክል ነው ወይ? የሚለው ባጣቃላይም የአለም የጤና ድርጅት ባስቀመጠው መስፈርት መሰረት ታይቶ ጥሩ ውጤት ካለው ወንድየው የመካንነት ችግር እንደሌለበት ምስክርነት ሊሰጠው ይችላል፡፡ ነገር ግን ውጤቱ ጥሩ ካልሆነ ምርመራው በአንድ ጊዜ አጋጣሚ የተደረገ በመሆኑና ምናልባትም ለቀጣይ የሚሻሻልበት ሁኔታ ስለሚኖር እንደገና ከአንድ ወር በሁዋላ ለምርመራ ይቀጠራል፡፡ ይህ ሁሉ ምርመራ ከተደረገ በሁዋላ እንደሁኔታው በህክምና የሚድንም የማይድንም ይኖራል፡፡

(ካለፈው የቀጠለ)
(ይህን አስተያየት ለጋዜጣ በሚያመች መልኩ ለመቃኘት ሞክሬያለሁ)

ባለፈው እትም እንዳስቀመጥኩት “የተረሳ ወራሽ” የተባለው መጽሐፍ መጠንጠኛ ፍለጋ ነው፡፡ ትውልድን ፍለጋና ትምህርትን ፍለጋ መሪ መሽከርክሪት ናቸው፡፡ መለወጥ፣ መፀፀትና ይቅርታ መጠየቅ፣ መራራትና ይቅርታ ማድረግ መፍትሔ ጭብጦች ናቸው (Resolution themes)። ይኸውም ትውልዶችን ማቀራረብ፣ ስህተትን የማረምና መጪውን ትውልድ የማነጽ ዓላማ ያለው አድርጌ እንዳየው አድርጐኛል፡፡ 

ምዕራፎቹን ስንመረምራቸው፤ ደራሲዋ የኤች አይ ቪን አደጋና ከቫይረሱ ጋር የመኖር ጥንካሬን እንደማጓጓዣ (leverage) በመጠቀም፤ (እንደጠቋሚ - ታሪክ (prologue) ከምናየው የመጀመርያ ምዕራፍ ውስጥ) ከዋናዋ ገፀ ባህሪ ጋር ታስተዋውቀናለች። በኋላ ላይ በዝርዝር የህይወት ውጣ ውረዷን የምናያት ወ/ሮ ትዝታን፤ ታገናኘናለች (“ትዝታ” የሚል ስም የሰዋዊ አገላለጽ ወይም ተምሳሌታዊ ስም መሆኑን በውል አናውቅም፡፡) ከእሷ ጋር የምናገኘው ሐኪሙዋ ዶክተር ግርማ፤ ትውልድ ያወደመው፣ ሥርዓት የጐዳው ባለሙያ ሲሆን “የሥራ ተነሳሽነቱ በኑሮ ጫና እየተጨፈለቀና ርህራሄው ከሰብአዊነቱ ውስጥ እየተሸረሸረ ሲወጣ ይሰማው ነበር፡፡ ዶ/ር ግርማ ውጪ በመሄድና የግል ሥራ በመሥራት መሃል የባከነ ህይወትን የሚወክል ገፀ - ባህሪ ሲሆን ያም ሆኖ እንደ ትዝታ ጠንካራ የዘመን - ሰለባዎችን የሚታደግ፣ ተስፋ የሚሰጥ ሰው ሆኖ ነው የሚገኘው፡፡ ይህ ሰው አንዱ የዘመን ጠባሳ ነው፡፡
ኢያሱ መምህር ነው፡፡ እንደ ትዝታ ዋና ገፀ - ባህሪ ነው፡፡ እንደ ዶክተር ግርማ እሱንም ህይወት አጐሳቁሎታል፡፡ ታስሯል፡፡ መካን እስኪሆን ድረስ ተገርፏል፡፡ ተፈቷል፡፡ ኑሮ አበሳጭቶታል። የባለታሪኳ የትዝታ አሳዳጊ ነው፡፡ ከህፃንነት ለአካለ - መጠን እስክትደርስ አሳድጓታል፡፡ በኋላ ግን በድሏታል፡፡ በሁለቱ መካከል የሚፈጠረው ግጭት የታሪኩ መላ - ሰውነት ነው፡፡ በኋላ የመጽሐፉ ቁልፍ ቁልፍ ገፀ - ባህሪያት እነ አብሮ - አደጉ አወቀ፣ ዲያስፖራው የለህወሰን፣ ጓደኛው ኤፍሬም በወጉ ተሰናስለው የምናገኛቸው እያሱ በሚያደርገው የትዝታን ፍለጋ ሂደት ውስጥ ነው። ይህን መሠረታዊ ግጭት ደራሲዋ ያቀረበችው እንዲህ ነው:-
ገፅ 24 ላይ እንዲህ ታሳየናለች
የትዝታ ሃሳብ
“ትዝታ በህይወት ጥሪ በተሞላ ዕድሜዋ ላይ ስለነበረች ወደ ዩኒቨርሲቲ ስትገባ አባቷን ከብቸኝነት ጋር አጋፍጣው መሄድ ስላልፈለገች ትዳር እንዲመሠርት የምታደርግበትን መንገድ ታሰላስላለች”
የእያሱ ሃሳብ
“…ጊዜው ያመጣውን ችግር አንድ እርምጃ ቀድሞ ግብግብ ሊገጥመው በማሰብ፣ ዕውነታው የተጋረደበትን መጋረጃ ቀድዶ ከታሪኳ ጋር ሊያላትማት ወስኗል፡፡ ውሳኔውንም በተግባር አረጋገጠው፡፡ ሀቁን ከፊት ለፊት አስቀምጦ የአንቺነትሽን እውነታ እነሆ ተቀበይ አላት፡፡ “እኔኮ አባትሽ አይደለሁም፡፡
የዚህ ግጭት ውጤትም የእሱ የፍቅር/የወሲብ/ ፍላጐትና እርካታ ሆነ!! ደራሲዋ ቀጥላ እንደምትነግረንም፤
“ለዓመታት የኖሩት አባትና ልጅ በአንድ አፍታ በተከሰተ ሰይጣናዊ ድርጊት ወደተለያየና ጭራሽ ወደማይቀራረብ ተቃራኒ አለም ተሰማሩ፣ ሁለቱም በየፊናቸው ነጐዱ፡፡
የትዝታ ውሳኔ
ቀስ በቀስም ህሊናዋ መካሪ ዘካሪ፣ ቀጪና ተቆጪ ሆኖ ተጋፈጣት፤ ከዚያም እራስሺን ፈልጊ ብሎ አዘመታት (ገጽ 29) ይሄ ማንነትን ፍለጋ ነው የመጽሐፉ መሽከንተሪያ!!
ደራሲዋ፤ ዶክተር ግርማ ለትዝታ በሚመክራት ምክር በኩል የምታስተላልፍልን መልዕክት ጠንካራ የህይወት ፍልስፍና ሲሆን ትዝታ ወደፊት እምትከተለውን እንድናስብ ያደርገናል፡፡ - “…ሁኔታዎች የፈጠሩትን ችግር መጋፈጥ እንጂ መሸሽ አይጠቅምም፡፡ ሽሽት የፍርሃት ውጤት ነው፡፡ አንዴ ሽሽት ከጀመርሽ ደግሞ ሁሉም ነገር አሳዳጅሽ ይሆናል፡፡ ማብቂያ ማቆሚያ የሌለው ሽሽት፣ መጨረሺያውም ሽንፈትና ውድቀት ነው፡፡ መቼም ውድቀት አማራጭሽ ይሆናል ብዬ አላስብም፡፡”
እያሱ ትዝታን የበደለበት ሁኔታ ሰብዓዊ ድክመት (Human folly የሚሉት ዓይነት) የፈጠረው፣ እሱ አፍቅሬያታለሁ የሚልበት፣ ከፍቅር ይልቅ የወሲብ ስሜት ክጃሎት (Sexual lust or desire) የሚንርበት ሁኔታ ነው ለማለት ይቻላል፡፡ ድርጊቱ ተዓማኒና ጥንካሬ እንዲኖረው አመክንዮው/ያነሳሳው ሁኔታ፤ ብርቱ ትንታኔ ቢሰጥበት መልካም ነበር፡፡ ቀስ በቀስ ያደገ ስሜት መሆኑን የሚያጠይቅ (justification የሚሰጥ) ማሠሪያ አንቀጽ ቢኖረው የገፀ - ባህሪውን ድርጊት እንድንዘጋጅበት ያደርገን ነበር፡፡ በተለይም በሁለኛው ምዕራፍ በወጉ የምናገኛት ዋናዋ ገፀ ባህሪ ትዝታ ግን ከእያሱ መለያ ሰበቧ ተዓማኒ ነው፡፡ ወደፊት የሚጠብቃትን ህይወት ለመጋፈጥ ቆርጣ ስትወጣ የምናይባት ወኔም ገፀ - ባህሪዋን በቅጡ የሚሸከም ነው፡፡ ለመማር ያላት ፍላጐት፣ ወላጅ አልባነትን መቋቋም፣ የማንነት ፍለጋን መጋተር፣ ማህበራዊ ኑሮን ማሸነፍ፣ ሥራ ፍለጋ፣ የኢኮኖሚ ችግር፣ ልጆች ማሳደግና ማስተማር…ከሁሉም በላይ ፍላጐቷን የማይረዳላት ማህበረሰብ ውስጥ መኖር (misunderstood እንዲሉ)፤ ለገፀ - ባህሪዋ በጠንካራ ድርና ማግ መሠራት ምስክር ነው፡፡
ሌሎች ገፀ ባህሪያት
ኤፍሬም የእያሱ ጓደኛ በዘመን - የታሰረ (ወይም ባሁኑ ዘመን አነጋገር “የተቸከለ” stuck in time) ገፀ ባህሪ ነው፡፡ ሚናው እየጐላ የሚሄደው ወደኋላ ላይ በመሆኑ ገፀ - ባህሪውን ገና ስናውቀው ፋይዳው ግራ ያጋባል፡፡ ዋለልኝ ከውጪ የመጣና የሸሸውን ማህበረሰብ ሊክስ የመጣ ዳያስፖሬ ነው፡፡
የእያሱ ሠራተኛ ብርቄ በቅጡ የተሳለች የቤት ሠራተኛ ባህሪ ናት፡፡ ሆኖም የወሰደችው ቦታ የበዛ ይመስለኛል፡፡ አጠር አድርጐ ፋይዳዋን ማሳየት ይቻል ነበር፡፡
አንድ እጅግ የማረከኝ ሃሳብ፤ እያሱ ወደ ወላጆቹ ቤት ጂጂጋ ሄዶ ከታሰሩት ጓዶቹ እነማ እንደሞቱና እነማን እንደተረፉ ለመመዝገብ መነሳቱ ነው፡፡ ታሪክን ለመፃፍ ትውልድን ለማስታወስ፣ደራሲዋ ያላትን ፍላጐት ለማርካት የጣረችበት ዘዴ ወይም መላ - ይመስለኛል፡፡ ደስ ብሎኛል፡፡
መጽሐፉ በእናትና ልጅ የተሞላ ነው፡፡ ልዩም፣ ማህበረሰብ -ተኮርም፤ የሚያደርገው ያ ነው፡፡ በማንኛውም ህብረተሰብ የችግር ገፈት ቀማሾች እናትና ልጅ ናቸው እንደማለት ነው መጽሐፉ ያሰመረባቸው! ባለታሪኳ ትዝታ የሁለት ልጆች እናት ናት፡፡ የቤት ሠራተኛዋ ብርቄ ባለልጅ ናት፡፡ የትዝታ እናት አራሷን ትዝታን ይዛ የመጣች ናት፡፡ ትዝታ ደሴ የኖረችባት እናት ልጆች አሏት፡፡ የዐወቀ ሚስት ባለልጅ ናት፡፡
የሺመቤት፣ ትልቁ ልጇ የተገደለና ከትንሽ ልጇ ጋር የምትኖር ነበረች…እናትና ልጅ!
እንግዲህ መጽሐፉን በውርድ ስናየው፡፡ የአንዲት ወላጅ አልባ ሴት ህይወት፣ በኤችአይቪ መያዝና በወጉ ከቫይረሱ ጋር ለመኖር መቻል፣ እያሱ የተባለው መምህር ዋናዋን ባለታሪክ ትዝታን በአደራ ማሳደግ (እናት ወ/ሮ መውደድ ቤቱ ድረስ መጥታ ያስረከበችው መሆኑ፤) አደራውን ለማሳካት ለወላጆቹ መስጠቱ፣ ባለታሪኳ አድጋ ወደሱ መምጣቷ፤ ለአካለ መጠን ስትደርስ ስለተኛትና ስለደፈራት ቤቱን ጥላ መጥፋቷ፣ የአሳዳጊዋ እያሱ መታሰር፣ የወጣቶች እጅ መስጠት፣ የእያሱ ከእስርና ከሞት የተረፉ ወጣቶችን መመዝገብ፣ በፋሲካ ዋዜማ የብዙ ወጣቶች መረሸን፣ ሰፊ መቼት ፈጥረው፤ እያሱና አዲሱ ትዳሩ፣ የእያሱ አወቀን ከልጁ ማገናኘት ድረስ ተጉዞ፣ የማራዘሚያ መድሃኒት መውሰድ የጀመረችውንና የኤች አይ ቪ ጉዳይ አስተማሪ የሆነችውን ትዝታን እስክናገኝ የሚዘልቀውንና የዳያስፖሬው የዋለልኝ የሞቱ ባለታሪኮችን ፍለጋ መምጣት፣ የእያሱ፣ የኤፍሬምና የየለህወሰን የተወሳሰበ ግንኙነት ተንተርሶ የየለህወሰን ማንነት መገለጥ፣ የትዝታ ወንድም ልጅ መገኘት፡፡ የታሪክ ፍሰቱን እንዲፈታተነን በሚሞክር መንገድ የሚወርድ ነው የትዝታ የነኤፍሬምና የአክስቶቿ ግንኙነትና የቤተሰብ ድርጅት በ3ኛው ሚሌኒየም ማቋቋም፤ ማክተሚያው ነው፡፡
ካለፈው የሥርዓት አውዳሚ እርምጃ በኋላ በተፈጠረው ሁኔታ ላይ የተመሰረተው የመጽሐፉ የግራና ቀኝ የፍትጊያ አቅጣጫዎች (war zones):- ወገን አልባነት፣ የማንነት እጦት፣ ሥር - አልባ መሆን፣ መገለል፣ መገፋት፣ መቀጨት፣ ሥራ - አጥነት፣ የትምህርት እጦት፣ የኢኮኖሚ ችግር ባንድ ወገን፡፡
በሌላ ወገን መለወጥ፣ ቁርጠኝነት፣ በራስ መቋቋም፣ ራስን - መቻል፣ ፀፀትንና መከፋትን መጽሐፍ በመፃፍ መወጣት፣ ጽንዓትና ትዕግስትን የያዘ ነው፡፡ እንደዋና የመጽሐፉ ውጤት ልናገኘው የምንችለው ቁም ነገር:- ስህተትን ተረድቶ ይቅርታ መጠየቅ፣ ይቅርታ ማድረግና ለቀጣይ ህይወት ተዘጋጅቶ መንገድ መቀየስ ነው፡፡
በመጽሐፉ መሀል መሀል የምናገኛቸውን ቁምነገሮች በንዑስ ርዕሶች አንዳንዶቹን ልነቁጥ :-
በወቅቱ ት/ቤት - የተማሪና መምህራን ግንኙነት
“ተማሪዎቹና መምህራኑ የመሰረቱት የጠበቀ ግንኙነት ወደኋላ በአገሪቱ ውስጥ ለተስተጋባው የትግል ጥሪ የጋራ ምላሽ እንዲሰጡ አድርጓቸዋል…ህይወት በራሱ ስጋት ሆነ - ከተሞች የሰላም መንፈስ ራቃቸው፡፡ በከተማው የተከሰተው ሁኔታም የእያሱንና የሌሎች መምህራንን የትግል ተሳትፎ በእጥፍ አጐለበተው፡፡ የትግል ሥልታቸውንም ለወጠው፡፡ በየዕለቱ የሚጐርፉትን ወጣት ተሰዳጆች በማስጠለልና ከአደጋ ጠብቆ በማቆየት ተግባር ተጠመዱ፡፡ አስተማማኝ መሸሸጊያ ወደሆነው የገበሬ መንደር ወጣቶችን ማሸጋገር የመምህራኑ የዘወትር ሥራ ሆነ፡፡” የእያሱ ገፀ - ባህሪ የተሳለው በዚህ ሚሥጥራዊ ክንዋኔ ውስጥ ነው እንግዲህ፡፡
የትውልዱ የጋራ ስሜት በሚከተሉት መስመሮች ይታያል
እያሱ ቤት፤ በእንግድነት የመጣችውን መውደድን ስለታቀፈችው ልጅ የሚጠይቅበት ሁኔታ፡-
“ልጅሽ ወንድ ነው ወይስ ሴት?”
“ሴት ናት” ህፃኗን በስስት ጐንበስ ብላ እያየች መለሰችለት፡፡
“የማናት? ማለቴ አባቷ ማን ነው?”
“የሁላችንም ናት፡፡ የእኔ፤ የአንተ፣ የትግሉ የዘመኑ ልጅ ናት” አለችው ፍርጥም ብላ፡፡
የትውልዱን የጋርዮሽ ስሜት ብቻ ሳይሆን መጽሐፉ የልጅቷን ማንነት ሚሥጥራዊ በማድረግ ቀጣይነቱን ያረጋግጥልናል፡፡ ፍለጋ እንድንቀጥልም ይገፋፋናል፡፡
ትዝታን የአባቷ መክዳት ጐድቷታል
ትዝታ እያለቀሰችና ውስጧ በቁጭት እየተቃጠለ፣ለትዳሯና ለልጆቿ ስትል የከፈለችውን መስዋዕትነት፣በባሏና በዘመድ አዝማዶቹ የደረሰባትን ግፍ በዝርዝር አስረዳችው (ገጽ 472)
ከመጽሐፉ ያገኘሁት ትምህርት
የእያሱ መረጃ የማሰባሰብ ሙከራ ለእኛ ትውልድ መልዕክት የሚያስተላልፍ ነው ብዬ ገምቼዋለሁ፡፡ ትውልዳችን የት ደረሰ፣ ምን ደረሰበት? ምን ተማርንበት? ለማለት ያለና የሞተውን፣ የጠፋውንና የተሰደደውን፤ መመዝገብ ለብዙ ታሪካዊ እሴት አስተዋጽኦ ያደርግ ይመስለኛል፡፡
ዘናና ላላ የሚያደርጉ ትዕይንቶች አለመኖር
ጽሑፉ ባለፈው እንዳልኩት የምሬትና የሐዘን ምርቅ የበዛበት በመሆኑ ዘናና ላላ የሚያደርጉ ትዕይንቶች (relief scenes) ያስፈልጉታል፡፡ የዚህ ዓይነት ትዕይንት አንድ ቦታ ብቻ ነው ያየሁት - ገጽ 459 ላይ የምናገኘው፡፡
እንደዋዛ ማዳበሪያ ሆኖ የገባው ዝናቡ ጭሮ ወይም ዝናቡ በርጮሌ ነው፡፡ ለአብነት እንየው:-
“ታዲያ ወደፊት እንዴት ላገኝህ እችላለሁ?” አለው የለህወሰን ከቦርሳው አውጥቶ አስር ብር እየሰጠው፡፡
“ግዴለህም አታጣኝም፤ ዝናቡ ጭሮ ወይም ዝናቡ በርጮሌ ብለህ ብትጠይቅ ማንም ያሳይሃል፤ ገንዘብ እንጂ ሰውና ችግር ፈልገው አጥተውኝ አያውቁም… ይልቅ መኪናው ላይ ላሳፍርህ” አለው፤ 10 ብሩን ግንባሩን አስነክቶ ወደ ደረት ኪሱ እያስገባ፡፡ የለህወሰን በልጁ አነጋገር አዝኖ ሌላ 10 ብር ጨመረለት፡፡ ልጁ በደስታ ዘለለ! አቀፈው፤ ሳመው፡፡ ካሣፈረው በኋላ የለህወሰን የሰው ብዛት ሲያንስበት ተበሳጨ፡፡ ዝናቡ ግን “አንተ ማሰብ ያለብህ ስለሰዓቱ ነው…አምስት ሰዓት እየሆነ አይደል…በዚህ ሰዓት የማይሆን ነገር የለም፡፡ ሾፌሩ ከነሸጠው ያላችሁትን ተሳፋሪዎች እንደ አምሳ ሰው በመቁጠር ተነስቶ እብስ ለማለት ይችላል” ይለዋል፡፡
መምህር አበጀ እና ትዝታ
አበጀ የትዝታ ባለውለታ - ብቸኛ ሠናይ ባህሪ ነው፡፡ ደሴ ወስዶ ት/ቤት ያስገባት እሱ ነው፡፡
እሱም ግን እንደ ዶ/ር ግርማና እንደ እያሱ በሚሰራው ሥራ ደስተኛ አልነበረም፡፡ (የሰራተኛው የሥራ ተነሳሽነት ማጣት አንዱ አንኳር ጉዳይ መሆኑን እዚህም እናያለን) ውጪ ድርጅት ሲቀጠር ቤተሰቡን ይዞ ወደ ወሎ ሄደ፡፡ ትዝታን ወደ ደሴ ይዟት የሄደው ለዚህ ነው፡፡ ይህም ነው የትዝታን ደብዛ ከእነ እያሱ የጠፋባቸው፡፡
የሀገራችን ማስታወቂያዎች
ደራሲዋ፤ ስለሀገራችን ማስታወቂያ ባህል እግረ መንገዷን ልታሳየን ሞክራለች፡፡ በገጽ 450 እንዲህ ትላለች - በየለህወሰን አስተሳሰብ ውስጥ ሆና “በቲቪ ማስታወቂያ ሁሉም ከማሳየት ይልቅ በመናገር ላይ የተመሰረቱ መሆናቸው ነው፡፡ ለዚህ ሁለት መነሻዎችን አሰበ
1) ምናልባት ምንጫቸው የቴአትር ጥበብ መሆኑና በወጣትነታቸው
በድራማ የኖሩ መሆናቸው
2) በልምድም በትምህርትም ከትያትር ጥበብ ጋራ ራሳቸውን ያጣበቁ ግለሰቦች ከድራማ ውጪ መልዕክት ማስተላለፊያ የሌለ ስለሚመስላቸው
(3ኛው)ና ዋንኛው፤ የህብረተሰቡ አንድ መልዕክት ከማየት ከሁለት ሦስት ሰው ለመስማት የመምረጡ ባህል ነው!
መጽሐፉ እንደመጀመርያ መጽሐፍ፣ እንደማሟሻ፣ ግዴታውን ተወጥቷል፡፡
እንደምክር
የገጽ ብዛት ለሚያስደነግጠው የዛሬ አንባቢ፣ ከዋናው ጉዳይ የራቁ በጣም የተዘረዘሩና የተደጋገሙ አንቀፆችን በማውጣት ብንተባበረው ደግ ነው፡፡ ማቀላጠፍ ማለት ነው፡፡
የገፀ - ባህርያት መብዛት የመጽሐፉን ሰንሰለት እንደሚያስረዝመው፣ አልፎ አልፎም ሊያደናግረው እንደሚችል ማስተዋል፡፡

Saturday, 03 August 2013 10:39

የትግራይ ጉዞ ማስታወሻ

ተናጋሪዋ ምድር

“ጋዜጠኝነት የተጀመረው አክሱም ውስጥ ነው”

የዛሬው ጉብኝታችን የሚጀምረው ከሳባ ቤተመንግሥት ነው። ከአክሱም ከተማ ምዕራባዊ አቅጣጫ፣ ትንሽ ወጣ ብሎ የሚገኘው የሳባ ቤተመንግሥት ልዩ ልዩ አገልግሎት ይሰጡ የነበሩ 42 ክፍሎች አሉት፤ ሌሎች አራት አብያተ መንግሥታትም አክሱም ውስጥ ተቀብረው እንደሚገኙ ተረድተናል፡፡ ከክርስቶስ ልደት በፊት በአገራችን ያን የመሰለ ህንጻ ይገነባ ነበር ብሎ ለማስረዳት ይከብዳል፤ ግን እውነት ነው፡፡ ራሱ ህንጻው ዛሬም በእማኝነት እንደቆመ ይገኛል - ቆሞ የሚገኘው ሙሉ ለሙሉ አለመሆኑን ግን አንዘንጋ፤ በቁፋሮ የተገኘ ነውና!
ከሳባ ቤተመንግሥት ፊት ለፊት የቆሙ፣ ያዘነበሉና የወደቁ በርካታ ሃውልቶች ይገኛሉ። ቦታውም የነጋዴዎችና የዕደ ጥበብ ባለሙያዎች መቃብር የነበረ መሆኑን የዘላቁ ቱሪዝም ልማት አስተባባሪ አቶ ቴዎድሮስ አብርሃም አስረድተውናል።
በንግሥተ ሣባ ቤተመንግሥት ውበትና በሥራው ውስብስብነት እየተደነቅን ወደ አክሱም ሰሜናዊ ምሥራቅ አቅጣጫ ተጓዝን፤ ትግራይ ውስጥ በጥንቃቄ መጓዝ ብቻ ያስፈልጋል፡፡ ጥንቃቄው ደግሞ ዕርባና የሌለው የሚመስል ድንጋይ፣ ውሃ፣ ወይም ጉብታ በአስደናቂ ታሪክ የተዋበ ሊሆን ስለሚችል ሳናየው እንዳያመልጠን ነው፡፡
አሁን ቅድመ ልደተ ክርስቶስ የተሠራውንና በሃገራችን የመጀመሪያ እንደሆነ የሚነገርለትን ማይሹምን እየጐበኘን ነው፤ “ማይሹም” ማለት “የሹም ውሃ” ማለት መሆኑን ተገንዝበናል፡፡ እንዲያውም “የአክሱም ሥያሜ የተገኘው ከዚሁ ነው” የሚሉም አሉ፤ ምክንያታቸው ደግሞ በአገውኛ ቋንቋ “አክ” ማለት “ውሃ” ማለት ሲሆን “ሱም” ደግሞ “ሹም ማለት ነው” የሚል ነው፡፡ “አክ” እና “ሱም” በአንድ ላይ “አክሱም” ይሆናል ማለት ነው፡፡
ለማንኛውም ግድቡ የንግሥቲቱ መዋኛ እንደነበር፣ አሁንም ለአካባቢው ነዋሪዎች ልዩ ልዩ አገልግሎት እንደሚሰጥ አስጐብኚያችን ነግረውናል፡፡ ግድቦቹ ሁለት ናቸው፤ የህጻናትና የአዋቂዎች መዋኛ፡፡ ግድቡ የመጀመሪያ መሆኑ ብቻ ሳይሆን የሚያስገርመው በርካታ አብያተ መንግሥትና አብያተ እምነት፣ እንዲሁም መኖሪያ ቤቶችና መቃብር ቤቶች ተቀብረው ሲገኙ ግድቡ ግን ከሶስት ሺህ ዓመታት በላይ በደለል ሳይሞላ እስካሁን መገኘቱ ነው፡፡
ከግድቡ ከፍ ብሎ ውሃ ከቦረቦረው የመሬት አካል አንድ የህንጻ ግድግዳ ይታያል፤ “እናንተ ቆፍራችሁ ባታወጡኝም በወራጅ ውሃ አጋዥነት እኔው እወጣና ምን እንደ ነበርኩ ለትውልዱ እመሰራክለሁ” የሚል ይመስላል፡፡ ከእሱ ፊት ለፊት ከሚገኝ የእርሻ መሬት ጫፍ ወደተቀለሰች ዛኒጋባ አስጐብኝያችን ወሰዱንና ሌላ ተአምር አየን፡፡
ከዛኒጋባዋ መሃል አንድ በሶስት ማዕዘን የተጠረበ ድንጋይ በኩራትም በትዝብትም በሚመስል አኳኋን ቆሟል፡፡ ሃውልቱን ያቆመው ኢዛና መሆኑን ራሱ ሃውልቱ ይመሰክራል፤ እንዲያውም ከቦታው ያነቃነቀው ሰው ዘሩ ሁሉ የተረገመ እንዲሆን ተጽፎበታል፡፡ በሃውልቱ ሶስቱም ማዕዘናት፤ በግዕዝ፣ በሳባ እና በግሪክ ቋንቋዎች የተጻፈ ተመሳሳይ መልእክት አለ፡፡
የሃውልቱ አጠራረብም ሆነ የተጻፈበት ቁም ነገር ከድንጋይነት ይልቅ ብራና አስመስሎታል። የቆመውም ኢዛና ኑብይ ወርዶ የገደለውን፣ የማረከውንና በአጠቃላይም ያገኘውን ድል የሚያበስረውን የጦር ሜዳ ዘገባ ይዞ ነው፡፡ ይህንን ምሥጢር ሳይና ስሰማ ትዝ ያለኝ ስለጋዜጠኝነት አጀማመር ሲነገረን የኖረው ምን ያህል ከእውነቱ የራቀ መሆኑን ነው፡፡
ብዙ ጊዜ ሲነገር የምንሰማው “የተማርነውም” ጋዜጠኝነት የተጀመረው አውሮፓ (ሮም) ውስጥ መሆኑን ነበር፤ ግን የእኛ አባቶች ገና ብራና እንኳ መፋቅ ሳይጀምሩ የጦርነት ዘገባዎችን ድንጋይ ላይ ያሰፍሩ ነበር፡፡ በመሆኑም የአገራችን የጋዜጠኝነት ምሁራን ርቃ ከምትገኘው ሮም ይልቅ ፊታቸውን ወደ አክሱም በማዞር ጥልቅ ጥናትና ምርምር ሊይደርጉ ይገባ ይመስለኛል፡፡ ለነገሩ ፈረንጅ ካልነገረን በቀር የራሳችን ሃቅ እውነት አይመስለንም፡፡ ይህ ክፉ ልክፍት ነው፡፡ እንዲያውም “ፊደል የመጣው ከሌላ አገር ነው” እያሉ የሚከራከሩ ሰዎችም አጋጥመውኛል፡፡ ግንኮ እኒያ ህያው ድንጋዮች የሚመሰክሩት እውነት ሌላ ነው፤ ተናጋሪዋ የትግራይ ምድር “ሹክ” የምትለን ምሥጢርም በእጅጉ የሚያኮራ ነው፡፡
ኢኖ ሊትማንን የመሰሉ አለም አቀፍ ምሁራን፤ የሃውልቶቹና ጥርብ ድንጋዮቹ ምሥጢር አማልሏቸው ወደ እኛ ይጐርፋሉ፤ በተቃራኒው እኛ ደግሞ ፈረንጅ እናመልካለን ወይም መመራመር ሳንከጅል የእነሱን መጻሕፍት ለመቃረም ወደ ፈረንጅ ሰፈር እንጋልባለን፡፡ በኔ እምነት ይህ ሐፍረት ነው፡፡ ፈረንጆች ግዕዙን ተምረው በሃውልቶቻችን እና በብራና መጻሕፍት ላይ በግዕዝ ቋንቋ የተጻፉትን ምሥጢራት ሃተታ ሰርተውባቸዋል፤ እየሠሩም ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ “ጊዘር” የተባለ ጀርመናዊ ምሑር፤ ከአራት ዓመት በፊት የአጼ ገብረ መስቀልን አጽም ማግኘቱን ይፋ አድርጓል፡፡ እኛ ግን ዛሬም እጃችንን አጣጥፈን የፈረንጅ ማረጋገጫ እንሻለን፡፡
እርግጥ ነው የአፄ ካሌብና የአፄ ገብረ መስቀል መካነ መቃብር አካባቢ፣ የአክሱም ዩኒቨርሲቲ የሥነ ስብእና የሥነ ምድር ምሑራን የምርምር ሙከራ እያደረጉ መሆኑን ተገንዝበናል፤ ይህ በእጅጉ ሊበረታታ የሚገባው ድንቅ ጅምር ነው፡፡
የአፄ ካሌብ መቃብር ወይም አፄ ካሌብ ለራሳቸው እንዳስገነቡት የሚነገርለትና በ6ኛው መቶ ክ.ዘመን ተሠራ የሚባለው መቃብር አሠራር ግሩም ነው፡፡ ጣራውም፣ ግድግዳውም ወለሉም ሆነ ሳጥኑ የተሠራው ከትላልቅ ጥርብ ድንጋዮች ነው፡፡ ይህን ስመለከት እኒያ ድንቅ ጥበበኛ እጆች፣ እኒያ እጅግ ጠንካራ ሰውነቶች የማውቃቸው ያህል በፊቴ ድቅን አሉና ቀናሁባቸው፤
መቃብሮቹ የተለያየ ቅርጽና መጠን አላቸው፤ አንዳንዶቹ በዋሻ አይነት ቅርጽ ተሠርተው ለቤተሰቡ ጭምር እንዲሆኑ የተገነቡ ናቸው፡፡ ሌሎች ደግሞ በመስቀል ቅርጽ ተሰርተው አራት ኪሶች አሏቸው፡፡ በአብዛኞቹ መቃብሮች ውስጥ የተገኙ ማስረጃዎች እንሚያስረዱት፤ የያኔዎቹ ወገኖቻችን ይቀበሩ የነበረው ድንጋዩን እንደ እንጨት እየጠረቡ በድንጋይ ሳጥን የመቃብር ፋካ መሥራት ነበር፡፡
የተጀመውም ያኔ ይመስለኛል፡፡
አንዱን የድንጋይ ሣጥን የጀርመን ተመራማሪዎች ለሁለት ቆርጠው ወደአገራቸው ሊወስዱት ሲሉ የአካባቢው ሕዝብ “ቅርሳችን ከቦታው ንቅንቅ አይልም” ብሎ አስቀርቶታል፡፡ ቀደም ሲል እንደጠቀስሁት ምርምሩ በሀገራችን ምሑራን መካሄድ አለበት ያልሁትም ሊከሰት የሚችለውን የዚህ ዓይነቱን ዘረፋ ለማስቀረት ስለሚረዳና ታሪካችንን ገልብጠው ለባዕድ እንዳያወርሱብን በመስጋት ጭምር ነው፡፡
ፈረንጆች እኮ እንኳን ግኡዙን ታሪካችንን እንደፈላስፋው ዘርዓያዕቆብ ያሉ ምርጥ አዕምሮዎችን ሊዘርፉን በእጅጉ ሞክረዋል፡፡ እናም “ሐይ” ባይ ያስፈልጋል፡፡ ለነገሩ እንኳን ከምድር ውስጥ ያለው ቅርሳችን ሊጠናና ሊታወቅ ቀርቶ፣ አዕላፍ ዘመናትን ተሻግሮ ዛሬም ሕያው የሆነው ትውፊታችን ገና አልተመዘገበም፡፡ የአውሮፓ በተለይ የግሪክና የሮማ፣ እንዲሁም የአፍሪካ የዕምነት ትውፊቶች በአግባቡ ተጠንተዋል፤ ተመዝግበውም ለትውልድ እየተላለፉ ናቸው፡፡ እኛ ግን ዛሬም ፈረንጅ ካልጻፈልን ጉዳዩን ከቁብ አንቆጥረውም፡፡
ለምሳሌ ከአክሱም ከተማ ወደ ሰሜን በግምት አራት ወይም አምስት ኪሎሜትር ርቀት ላይ አንድ ቀጥ ብሎ የቆመ ሹል ተራራ አለ፤ የቦታው ስም “ተመን ዘውገ (የዘንዶ ወገን)” ይባላል፡፡ አካባቢው ደግሞ “አድ ጸሐፊ (የጸሐፊ አገር)” በመባል ይታወቃል፡፡ ከዚያ ተራራ ጋር የተያያዘ አንድ ትውፊት ይነገራል፡፡
በጥንቱ ዘመን ዘንዶ ይመለክ ነበር አሉ፤ ዘንዶው በዚያ ተራራ ይኖር ነበር፤ ውሃ መጠጣት ሲያምረው ጅራቱን በተመን ዘውገ (ተራራ መሆኑን ልብ ይሏል) ያስርና ከመረብ ወንዝ ይጠጣ ነበር የሚል ትውፊት አሁንም ድረስ በሰፊው እንደሚነገር ከአካባቢው ነዋሪዎች ተረድተናል፡፡
ጉዳዩ “ራ” ከምትባለው የግብጽ የፀሐይ አምላክ ጋር፣ ወይም ከኬንያዎቹ የዝናብ አማልክት ጋር ይመሳሰላል፡፡ “ዘንዶ ወይም እባብ ዝናብንና ቀስተደመናን የመፍጠር ችሎታ ያለው ነው፤ ቆዳውን በየጊዜው በመቀያየር ስለሚኖርም ዘለዓለማዊ ነው” ተብሎ ይታመን እንደነበር “አፍሪካን ሚቲዮሎጂ” የተባለ መጽሐፍ ያስረዳል፡፡
የእኛው የዘንዶና የዕምነት ትውፊት ግን ፕሮፌሰር ስርግው ሐብለሥላሴ “የኢትዮጵያ ታሪክ” በተባለ መጽሐፋቸው፡፡ በአጭሩ ከመነካካታቸውና አቶ ተክለ ጻድቅ መኩሪያ “ከጣኦት አምልኮ ወደ ክርስትና” በሚለው መጽሐፋቸው በአጭሩ ከመዳሰሳቸው በቀር ራሱን ችሎ አልተጠናም፡፡ ሕዝቡ ግን አሁንም ትውፊቱን እየተቀባበለ ለልጆቹም እየቀበለ ነው፤ ሳምንት እንገናኝ፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ዘማሪ ወፍ በወጥመድ ተይዛ በቆንጆ ድምጽዋ ትዘምራለች፡፡ ድምፁዋ በጣም ከማማሩ የነሳ ሌሎች ወፎች ሁሉ ፀጥ ብለው ያዳምጡዋታል፡፡
“ስበር እውላለሁ፡፡
ስከንፍ አረፍዳለሁ፡፡
ማን ይየኝ ማን ይስማኝ
መች እጨነቃለሁ?
የምሮጥ ለራሴ፣
የመኖር ለራሴ፣
ይድከመኝ ይመመኝ፣
ራሴ ነኝ ዋሴ፡፡
ሰው ግን ይከፋዋል፣
ጥላዬ ሲያርፍበት
ላይከብደው ላይጐዳው፣
ድንገት ባለፈበት፡፡
ሊያጠምደኝ ይለፋል፤ ጉዳዩ አይገባኝም፡፡
ወፍ ይዞ በማሰር፣ ምን እንደሚጠቀም?
ሽቦ - ቤት ባልገባም፤ መዘመሬ አይቀርም…
ሽቦ ቤት ብገባም መዘመሬ አይቀርም!!”
ይህን መዝሙሯን ሁሌ ማታ ማታ ስታሰማ የሌሊት - ወፍ መጥታ በጥሞና ታዳምጣታለች፡፡ አንድ ቀን እንዲህ ስትል ጠየቀቻት፤
“እመት ወፊት?”
“እመት” አለች ወፊት፡፡
የሌሊት ወፍ - “ሁሌ ስትዘምሪ እሰማሻለሁ”
ወፊት - “አዎን”
የሌሊት ወፍ - “ለተኙት ወፎች?”
ወፊት - “አይደለም”
የሌሊት - ወፍ- “ታዲያ ለማነው?”
ወፊት - “ለራሴ!” አለች ፍርጥም ብላ፡፡
የሌሊት ወፍ - “ግን ሁሌ ማታ ማታ ነው የምትዘምሪው?”
ወፊት - “አዎን”
የሌሊት - ወፍ - “ለምን ቀን ቀን አትዘምሪም”
ወፊት - “ቀን ቀን ችግር ነው፡፡ ከዚህ ቀደም ቀን ቀን ስዘምር የሰው ልጅ ሰማኝ፡፡ ‘መጥቼ አጠገብሽ ቁጭ ብዬ ላድምጥሽ፡፡ በጣም ቆንጆ ነው የምትዘምሪው’ አለኝ፡፡
እሺ ብዬ አጠገቡ ሆኜ ስዘምር ድንገት ቀጨም አደረገኝ፡፡ ይሄው እዚህ የሽቦ እሥር ቤት ውስጥ ከተተኝ!”
የሌሊት ወፍም፤ “እመት ወፊት፤ ሰው ጠላትሽ መሆኑን ማወቅሽ ድንቅ ነው፡፡ ግን አንድ ነገር ልብ በይ። አንዴ እሥር ቤት ከገባሽ በኋላ ቀንም ዘመርሽ ማታም ዘመርሽ ለውጥ የለውም፡፡ ሰውዬው ለሁለተኛ ጊዜ ሊያጠምድሽ አይመጣም፡፡ ምክንያቱም በእጁ ነሻ!” አለቻት
* * *
የማናቸውም ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ቁልፍ ጉዳይ ጊዜ ማወቅ ነው (timing)፡፡ ከዕለቱ አስቀድሞም መንቀሳቀስ፣ ዕለቱ ካለፈም በኋላ መንቀሳቀስ፣ ችግር ላይ ይጥላል፡፡ ትክክለኛ የጊዜ ምጣኔ ያለው የፖለቲካ ሰው፤ ብዙውን የጨዋታውን ሰዓት በእጁ ያስገባ ኳስ ተጨዋች እንደማለት ነው - የሚቀረው ጐል ማግባት ብቻ ነው!
የቅርጫት ኳስ ተጨዋችን ምሳሌ ብናደርገው ደግሞ የመጨረሻዋ ሶስት - ሴኮንድ - ክልል በምትባለው ሳጥን ውስጥ ከገባ፤ ያለው ዕድል ወደ ቅርጫቱ መወርወር ብቻ ነው፡፡ ከዘገየ ቀለጠ፡፡ “ቦታን ደግመን ልንይዘው እንችላለን፡፡ ጊዜን ግን በጭራሽ ደግመን አናየውም” እንዳለው ነው ናፖሊዮን ቦናፓርት፡፡ የጥንቱ የጧቱ ፖለቲከኛ ሌኒንም “Seize the time, seize the gun” ይለዋል፡፡ “ጊዜን ያዝ፣ ጠመንጃህን ጨብጥ!” እንደማለት ነው፡፡
“ለድል የሚያበቃህ፤ አደለም ጀግንነት
አዛዡ ጊዜ ነው፣ በጊዜ እወቅበት!” እንዳለው ነው የአገራችን ገጣሚ፡፡
ባለፈው ሥርዓት ዝነኛ ከነበሩት መፈክሮች አንዱ፤ “ማፍረስ ቀላል ባይሆንም መገንባት የበለጠ ከባድ ነው” የሚል ነበር፡፡ ዕውነት ነው፡፡ የምናፈርሰውን በጊዜ ማፍረስ፣ እምንገነባውን በጊዜ መገንባት፣ ፍፁም ብልህነት ነው፡፡ በእርግጥም ከማፍረስ ይልቅ መገንባት የበለጠ ከባድ ነው፡፡ የምናፈርሳቸው ቤቶች የሚተኩበትን ህንፃ በማሰብ ብቻ ከተጓዝን፣ የሚያመጣውን አፍራሽ ውጤት (Repercussions) ልብ ሳንል እንቀራለን፡፡ ደምረን ማስተዋል አለብን፡፡ “ነገሮች ምድር ላይ ሰላም ሆነው ይታያሉ፤ እሳቱ ያለው ከሥር ነው” ይላሉ ቱርኮች፡፡ ምንጊዜም ተናጠል ሁነቶች አድገው አስተፈሪ የማይሆኑ ይመስሉናል፡፡ ድምር ውጤታቸውን ግን ዐይን ያለው ነው የሚያይ፡፡ ስለዚህ እንይ! እንይ! እንይ! የቅሬታዎች ሥርና ክር፤ የቱን ያህል እንደሚርቅና የቱን ያህል እንደሚከር እናስተውል፡፡ ካፈረስን በኋላ የፈረሰባቸው ምን ሆኑ? በፈረሰው ቦታ ላይ ምን ተካን? ብለን ደጋግመን እንጠይቅ!
“ብዙዎች የነዳጅ ታንካቸውን ለመሙላት ሲጨነቁ ሌሎች በዓለም ዙሪያ ያሉ ደግሞ ሆዳቸውን ለመሙላት ይታገላሉ፡፡ ይሄ ደግሞ ከቀን ቀን እየባሰ፣ ከቀን ቀን እየከፋ ነው የመጣው” ይላሉ፤ የዓለም ባንኩ ፕሬዚዳንት ሮበርት ዞሊክ፡፡ (ዳምቢሣ ሞዮ)
የኑሮ ልዩነት ክፍተት እየሰፋ፣ ጥቂቶች እየተመቻቸው ብዙዎች እየተራቡ የሚሄዱበት ሁኔታ ውሎ አድሮ ጦሱ አይጣል ነው፡፡
ዛሬ ሰላም የሚመስለን ጐዳና ነገ በብሶተኛ ይሞላል፡፡ ጐርፉ መቼ እንደሚሞላ አናውቅም፡፡ የጐርፉን ምንጭ ግን እናውቃለን፡፡ እሱን ለማድረቅም እንችላለን - ልብ ካለን! ነገሮችን በትክክል አይተን በትክክል ካልፈታናቸው፣ በተለይ ትክክለኛ የጊዜ አጠቃቀም ከሌለን፤ እያደር ከድጡ ወደማጡ እንዳንሄድ፣ ወይም እንደዱሮው አነጋገር “ወጣ ወጣና እንደሽምበቆ ተንከባለለ እንደሙቀጫ” ዓይነት ሁኔታ እንዳይገጥመን፤ በእጅጉ መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ መተው ያለብንን መተው፣ በጊዜ መራመድ ያለብንን መራመድ ያሻናል፡፡ አለበለዚያ የትግሪኛው ተረት እንደሚነግረን፤ “ዘወር ካለማለት ነገሩ ሰፋ፣ ቶሎ ካለመሻገር ጐርፉ ሞላ”፤ ማለት ይሆናል ትርፋችን፡፡

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) በአገሪቱ የተለያዩ ከተሞች በሚገኙ አመራሮችና አባላቱ ላይ በገዢው ፓርቲ የድብደባ፣ የእስርና የግል ሚስጥር መበርበርና በተደራጀ ሁኔታ የመዝረፍ ድርጊት እየተፈፀመ መሆኑን ገለፀ፡፡
ፓርቲው “ህጋዊና ሠላማዊ ትግላችን በህገወጥ የአፈና ስልት ሊደናቀፍ አይችልም” በሚል ትናንት ባወጣው መግለጫ ላይ፤ መንግስት አንድነት ፓርቲን በሀሰት ፕሮፖጋንዳ ከማጣጣልና ያለ አግባብ ከአክራሪነት ጋር ለማቆራኘት ከመስራት አልፎ ሠላማዊ ሠልፎችና ህዝባዊ ስብሰባዎቹ እንዲደናቀፉ አፈና እያደረገበት እንደሚገኝ ገልጿል፡፡
በወላይት ሶዶና በመቀሌ የፓርቲው አመራሮችና አባላት ላይ የመደብደብ፣ የማሰር፣ የግል ሚስጥር የመበርበርና በተደራጀ ሁኔታ የመዝረፍ ድርጊት እንደተፈፀመበት ጠቅሶ፣ ፖሊስ ድርጊቱን አይቶ እንዳላየ ማለፉን ገልጿል፡፡
ፓርቲው በነገው እለት በጂንካ፣ በአርባ ምንጭ፣ በመቀሌ፣ በወላይታ፣ በባህርዳርና በአዲስ አበባ የሚያካሂዳቸውን ሠላማዊ ሰልፎችና ህዝባዊ ስብሰባዎችን ለማደናቀፍ በገዢው ፓርቲ አፈናና ወከባ እየተፈፀመበት እንደሚገኝም ጠቁሟል፡፡
አንድነት ህግን መሰረት አድርጐ እየተንቀሳቀሰ በመሆኑ በነገው ዕለት ሊካሄዱ የታሰቡት ሁሉም ሠላማዊ ሰልፎችና ህዝባዊ ስብሰባዎች በተያዘላቸው እቅድ መሰረት እንደሚከናወኑና ህጋዊ እርምጃው በህገወጥ አፈናው ምክንያት እንደማይቀለበስ በመጥቀስ፣ መላው አገሪቱ ህዝብ በነቂስ ወጥቶ የታፈነ ድምፁን እንዲያሰማ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡

በህንዳዊው መምህርና ፀሐፊ ሚ/ር ጆሴፍ ፍራንሲስ የተዘጋጀ “የድንቂቱ ኢትዮጵያ ድንቃድንቆች” (“This is Ethiopia – A Book of Fascinating Facts”) የተሰኘ ስለ ኢትዮጵያ የተለያዩ ድንቅ መረጃዎችን ያካተተ አዲስ መፅሐፍ የፊታችን ረቡዕ ከምሽቱ 12 ሰዓት ሚኒስትር ዴኤታ ሙሉጌታ ሰኢድ ዳምጠው በተገኙበት በካፒታል ሆቴል ይመረቃል፡፡
መፅሐፉ፤ ኢትዮጵያን ልዩ የሚያደርጋትን ከ245 በላይ መረጃዎች ያካተተ ሲሆን የተዘጋጀበትም ዓላማ፤ በተለይ የውጭ አገር አንባቢያንና ዳያስፖራዎች፣ ስለ ኢትዮጵያ መረጃዎችን በቀላሉና በአጭሩ እንዲቀስሙ ለማድረግ ነው ተብሏል፡፡ በመፅሐፉ ጀርባ ላይ አስተያየታቸውን ያሰፈሩት የታሪክ ባለሙያው ፕ/ር ሪቻርድ ፓንክረስት፤ “ስለ ኢትዮጵያ ብዙ የማናውቃቸው አስደናቂ ነገሮች መኖራቸውን… መፅሃፉ እንድንገነዘብ ያደርገናል፡፡ መፅሃፉ ያካተታቸው መረጃዎች ብዙ አንባቢዎችን ሊያስደምሙ የሚችሉ ናቸው” ብለዋል፡፡
መፅሃፉ በእንግሊዝኛና በአማርኛ የተዘጋጀ ሲሆን ትርጉሙን የሰራው ደራሲ አማረ ማሞ ነው፡፡ የውስጥ ገፆቹ ሁሉ ባለቀለም ሆነው የተዘጋጀው “የድንቂቱ ኢትዮጵያ ድንቃድንቆች” መጽሐፍ መረጃዎች በተዋቡ ምስሎች ተደግፈው ቀርበውበታል፡፡ ላለፉት 30 ዓመታት ኢትዮጵያ ውስጥ በመምህርነት ያገለገለው ሚ/ር ጆሴፍ ፍራንሲስ፤ ከዚህ ቀደም “የአድዋ ጦርነት”፣ “ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ” እና “የአፄ ቴዎድሮስ ልጅ፣ ልዑል ዓለማየሁ” የተሰኙ የልጆችና ወጣቶች መፃህፍትን አሳትሟል፡፡

“ቦሌ ፒኮክ ጋ ጠብቂኝ” በተሰኘው የሰለሞን ፍስሀ መጽሐፍ ላይ ነገ ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቤተመዛግብት እና ቤተመጻሕፍት አዳራሽ ውይይት እንደሚካሄድ ሚዩዚክ ሜይደይ አስታወቀ፡፡ ውይይቱን የሚመሩት ሃያሲ እና የወግ ጸሐፊ መስፍን ሀብተማርያም እንደሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

የጋዜጠኛና ገጣሚ ተስፋዬ ገብረማርያም “የማይሆን ዓለም” የተሰኘ ግጥሞች፣ አጫጭር ልቦለዶች እና ወግ የተካተቱበት መጽሐፍ ነገ በሐገር ፍቅር ትያትር ቤት ትንሿ አዳራሽ እንደሚመረቅ “ሀሳብ መልቲሚዲያ” አስታወቀ፡፡ በ62 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፣ በ20 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ጋዜጠኛና ገጣሚ ተስፋዬ በ“ኢትዮ ቻናል” ጋዜጣ ማህበራዊ ጉዳዮች አምድ ጸሐፊነቱና በዛሚ 90.7 ኤፍ ኤም ሬዲዮ በሚያቀርበው “ድርሻችን” የተሰኘ በአካል ጉዳተኞች ላይ ያተኮረ ፕሮግራም ይታወቃል፡፡

“ዜማ ቃል” የተሰኘ ወርሃዊ የጥበብ ምሽት ሐሙስ ከቀኑ 10፡30 ጀምሮ  በሐገር ፍቅር ትያትር ቤት ትንሿ አዳራሽ እንደሚቀርብ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ ለአንድ ዓመት በሚዘልቀው ዝግጅት፣ የገጣሚያን፣ ጸሐፍትና ኮሜዲያን  ሥራዎች የሚቀርብበት ሲሆን የመግቢያ ዋጋው በነፍስ ወከፍ 50 ብር እንደሆነ ዝግጅቱን የሚያስተባብረው ፈለቀ ካሳ ጥንድ ፕሮሞሽን  ጠቁሟል፡፡ 

በዶ/ር ሱዛን ጄፈርስ የተፃፈው “Feel the Fear and Do it Anyway” የተሰኘ መፅሃፍ፤“ፍርሃትን ማሸነፍ” በሚል ርእስ በቢኒያም አለማየሁ ተተርጉሞ ለንባብ በቃ፡፡ መጽሐፉ አሉታዊ አመለካከትን ስለማስወገድ፣ ውሳኔዎችን በሥራ ስለ መተግበር፣ ፍርሃትን ስለ ማጥፋት እና ሌሎች ተያያዥ ቁም ነገሮችን የያዘ ነው፡፡ 192 ገፆች ያሉት መፅሃፉ፤ ዋጋው 40.50 ብር ነው፡፡
በሌላም በኩል “በአራጣ የተያዘ ጭን” የተሰኘ የአጫጭር ልቦለዶች መድበል ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ በዮፍታሔ ካሳ የተደረሰው መጽሐፍ፤ በ233 ገፆቹ አስራ ዘጠኝ አጫጭር ልቦለዶች ይዟል፡፡ በኤች ዋይ ኢንተርናሽናል ማተሚያ ቤት የታተመውን መጽሐፍ፤ ሊትማን ጀነራል ትሬዲንግ የሚያከፋፍለው ሲሆን ዋጋውም 46.99 ብር ነው፡፡
በተመሳሳይ “ከመለስ ሞት በስተጀርባ” የተሰኘ መጽሐፍ በዚህ ሳምንት ለንባብ በቃ፡፡ መፅሃፉ በኢትዮጵያ፣ በግብፅ፣ በአባይ ግድብ፣ በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ እና ሌሎች ጉዳዮች ዙርያ ያጠነጥናል፡፡ በ70 ገጾች የተዘጋጀው መጽሐፉ፤ ለገበያ የቀረበው በ32 ብር ነው፡፡ በመፅሃፉ ውስጥ ከተካተቱት ፎቶግራፎች መካከልም በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግስት የሃምሳ ብር ኖት ላይ የወጣው የአባይ ግድብን የሚያሳይ ምስል ይገኝበታል፡፡