Administrator

Administrator

Saturday, 19 December 2015 09:46

የዘላለም ጥግ

(ስለ ሰላም)

• መጀመሪያ ከራስህ ጋር ሰላም ፍጠር፤
ከዚያ በኋላ ለሌሎች ሰላምን ማምጣት
ትችላለህ፡፡
ቶማስ ኤ ኬምፒስ
• ዓይን ላጠፋ ዓይኑን ማጥፋት የሚለው ህግ
መጨረሻው መላውን ዓለም ዓይነስውር
ማድረግ ነው፡፡
ማሃትማ ጋንዲ
• ሰላም በሃይል ሊጠበቅ አ ይችልም፤ ሰላም
ሊሰፍን የሚችለው በመግባባት ብቻ ነው፡፡
አልበርት አነስታይን
• ሰላም የግጭት አለመኖር አይደለም፤
ግጭትን በሰላማዊ መንገድ የመፍታት
አቅም ነው፡፡
ሮናልድ ሬገን
• በሰላም አምናለሁ፤ በይቅርባይነት
አምናለሁ፡፡
ማላላ ዩሳፍዛይ
• ከራሷ ጋር ሰላም የፈጠረች አፍሪካን
አልማለሁ፡፡
ኔልሰን ማንዴላ
• ሁላችንም በሰላም እንኖር ዘንድ ሁላችንም
ሰላምን መፍጠር አለብን፡፡
ዣን በርትራንድ አሪስቲዴ
• መላዕክት የሚዘምሩት የመጀመሪያ ነገር
ሰላምን ነው፡፡
ጆን ኬብሌ
• የሰው ልጅ ማስታወስ ያለበት ሰላም
እግዚአብሔር ለፍጡራኑ የሚያበረክተው
ስጦታ አለመሆኑን ነው፤ ሰላም አንዳችን
ለሌላችን የምናበረክተው ስጦታ ነው፡፡
ኢሊ ዊስል
• ሰላምና ፍትህ የአንድ ሳንቲም ሁለት
ገጽታዎች ናቸው፡፡
ድዋይት ዲ. ኢዘንሃወር
• ጦርነትን ማወጅ የለብንም ማለት ብቻ
በቂ አይደለም፤ ሰላምን መውደድና
መስዋዕትነት መክፈልም ይናርብናል፡፡
ማርቲን ሉተር ኪንግ
• ሰላምን እናፈቅራለን፤ ነገር ግን በማንኛውም
ዋጋ የተገኘ ሰላምን አይደለም፡፡
ዳግላስ ዊሊያም ዴሮልድ
• ተስፋ ልክ እንደ ሰላም ነው።
ከእግዚአብሔር የሚበረክትልን
ስጦታ አይደለም፡፡ አንዳችን ለሌላችን
የምናበረክተው ስጦታ ነው፡፡
ኢሊ ዊስል
• ከጦርነት አውድማ ወደ ሰላም ጠረጴዛ
ለመድረስ ረዥም መንገድ ተጉዣለሁ፡፡
ሞሼ ዳያን

  የአይሲሱ መሪ አቡበከር አል ባግዳዲ ሁለተኛ ደረጃን ይዘዋል
    በአለማችን በየአመቱ ስማቸው በክፉም ሆነ በደግ በስፋት የተነሳና አነጋጋሪ የሆኑ ግለሰቦችን እየመረጠ ይፋ የሚያደርገው ታዋቂው ታይም መጽሄት፣ የጀርመን መራሄ መንግስት አንጌላ መርኬልን የ2015 የታይም መጽሄት የዓለማችን ተጽዕኖ ፈጣሪ በማለት መምረጡን አስታወቀ፡፡
ታይም መጽሄት ረቡዕ ዕለት በድረ-ገጹ ይፋ ባደረገው መረጃ እንዳስታወቀው፣ ለዘንድሮው የታይም መጽሄት የአመቱ ምርጥ ሰው ምርጫ የመጨረሻ ዙር ከደረሱት ስምንት ዕጩዎች መካከል የመጽሄቱን አዘጋጆች አብላጫ ድጋፍ ያገኙት አንጌላ መርኬል አሸናፊ በመሆን ተመርጠዋል፡፡
ባለፉት 29 አመታት የታይም መጽሄት የአመቱ ምርጥ ለመባል የበቁት ብቸኛዋ ሴት የሆኑት አንጌላ መርኬል በዘንድሮው አመት በዩሮዞን ከተከሰተው የኢኮኖሚና የስደተኞች ቀውስ ጋር በተያያዘ ሰፊ የመገኛኛ ብዙሃን ሽፋን ያገኙ መሪ ሆነው መዝለቃቸው ለመመረጥ እንዳበቃቸው ተነግሯል፡፡
በዕጩነት ከቀረቡት ግለሰቦች መካከል አለማችንን በሽብር ተግባሩ እያመሳት የሚገኘው የአሸባሪው ቡድን አይሲስ መሪ አቡበከር አል ባግዳዲ ሁለተኛውን ደረጃ ሲይዙ፣ አነጋጋሪው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የሪፐብሊካን ፓርቲ ዕጩ ዶናልድ ትራምፕ ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል ተብሏል፡፡
የኢራኑ ፕሬዚዳንት ሃሰን ሩሃኒ፣ እንዲሁም አይሲስ የተባለውን የሽብር ቡድን አጠፋለሁ ብለው ጦራቸውን ያዘመቱት የሩስያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲንም በእጩነት ቀርበው ነበር፡፡
ባለፈው አመት የታይም መጽሄት ምርጥ ተብለው የተመረጡት በምዕራብ አፍሪካ አገራት የተከሰተውን የኢቦላ ቫይረስ በቁጥጥር ስር ለማዋል ያላሰለሰ ጥረት ያደረጉ ባለሙያዎች እንደነበሩ ያስታወሰው መጽሄቱ፣ በ2013 ደግሞ የሮማው ሊቃነ ጳጳስ ፖፕ ፍራንሲስ ተመርጠው እንደነበር አክሎ ገልጧል፡፡
ታይም መጽሄት የአመቱ ምርጦቹን መምረጥ የጀመረው እ.ኤ.አ በ1927 ሲሆን በወቅቱ የተመረጡትም ቻርለስ ሊንድበርግ የተባሉ አውሮፕላን አብራሪ እንደነበሩ መጽሄቱ አስታውሷል።
ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ፣ ማህታማ ጋንዲ፣ አዶልፍ ሂትለርና ኦባማን የመሳሰሉ የአገር መሪዎች፣ ፖለቲከኞችና ታዋቂ ግለሰቦች ከዚህ ቀደም የታይም መጽሄት የአመቱ ምርጦች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

 - ማሻሻያው ድጋፍ ካገኘ፣ ካጋሜ ለመጪዎቹ 19 አመታት በስልጣን ላይ ሊቆዩ ይችላሉ
    የሩዋንዳው ፕሬዚዳንት ፖል ካጋሜ በ2017 በሚካሄደው የአገሪቱ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ላይ እንዲሳተፉ ለማስቻል ታስቦ በህገ መንግስቱ ላይ የተደረገውን ረቂቅ ማሻሻያ በተመለከተ በመጪው ሳምንት ህዝበ ውሳኔ እንደሚደረግ ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በህገ መንግስቱ ላይ ሊደረግ የታሰበው ማሻሻያ በህዝበ ውሳኔው አብላጫ ድጋፍ ካገኘ፣ ፕሬዚዳንት ፖል ካጋሜ እስከ 2034 ድረስ በስልጣን ላይ መቆየት የሚችሉበት ዕድል ይፈጠርላቸዋል ያለው ዘገባው፣ የአገሪቱ ሴኔትም ፕሬዚዳንቱን በስልጣን ላይ ለማቆየት ታስቦ የተዘጋጀውን የህገ መንግስት ማሻሻያ ባለፈው ወር እንደተቀበለው አስታውሷል፡፡
አሜሪካ በ2017 የስልጣን ዘመናቸው ለሚያበቃው ለሩዋንዳው ፕሬዚዳንት ፖል ካጋሜ፣ #እባክዎት በሰላም ስልጣንዎን ይልቀቁና ለአካባቢው አገራት መንግስታት አርአያ ይሁኑ” ስትል ጥሪዋን ብታስተላልፍም፣ ካጋሜ ግን የአሜሪካንም ሆነ የሌሎች አገራትን መሰል ጥያቄ፣ በምስራቅ አፍሪካ አገራት የውስጥ ጉዳዮች ላይ የሚደረግ ጣልቃ ገብነት ነው ሲሉ ማጣጣላቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
አጃንስ ፍራስ ፕሬስ በበኩሉ÷ የህገ መንግስት ማሻሻያው በመጪው ሳምንት በሚደረገው ህዝበ ውሳኔ ድጋፍ አግኝቶ የመጽደቅ ዕድሉ ከፍተኛ ነው ሲል ዘግቧል፡፡

ለ700 ጊዜያት ያህል ታጥቦ፣ አገልግሎቱን አላቋረጠም
    ኪዮሴራ የተባለው የጃፓን የሞባይል አምራች ኩባንያ በአለማችን የስማርት ፎን ታሪክ በአይነቱ የመጀመሪያው የሆነውን በውሃና በሳሙና መታጠብ የሚችል ዲንጎ ራፍሪ የተሰኘ አዲስ የሞባይል ቀፎ አምርቶ ትናንት በገበያ ላይ ማዋሉን ሪያሊቲ ቱዴይ ድረገጽ ዘገበ፡፡ ምንም እንኳን ሶኒ ኩባንያን የመሳሰሉ የሞባይል አምራቾች ከዚህ ቀደም ውሃን መቋቋም የሚችሉ ሞባይል ስልኮችን ቢያመርቱም፣ ሞባይሎቹ ሳሙና ከነካቸው የሚበላሹ ነበሩ ያለው ዘገባው፣ ኪዮሴራ ያመረተው አዲስ ሞባይል ግን የሳሙና አረፋ ውስጥ ተዘፍዝፎ ቢውል አይበላሽም ብሏል፡፡
“ይህንን በአይነቱ ልዩ የሆነ ሞባይል ስልክ ያመረቱት የኩባንያችን ተመራማሪዎች፣ የስልኩን ብቃት ለማረጋገጥ ከ700 ጊዜያት በላይ ያጠቡት ሲሆን አንዳችም ችግር ሳይፈጠርበት አገልግሎት መስጠት መቀጠሉን አረጋግጠዋል” ብለዋል የኩባንያው ቃል አቀባይ፡፡ 465 ዶላር የተተመነለት ይህ የሞባይል ስልክ፣ በተለይም ልጆች ለሚበዙባቸው ቤተሰቦች ታልሞ የተመረተ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ ሞባይሉ ውሃና የሳሙና አረፋን መቋቋም የሚችል ሽፋን ያለው መሆኑንና፣ ስፒከሮቹን ጨምሮ የተገጠሙለት አካላት በሙሉ በፈሳሽ የማይበላሹ መሆናቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡

 ፔኔዛ በተባለችው የሩስያ ከተማ የሚንቀሳቀሰው ኮሙኒስት ፓርቲ፤ አምባገነኑን የቀድሞው የሩስያ መሪ ጆሴፍ ስታሊንን ለመዘከርና ብዙዎች እንደሚሉት ሰውዬው አምባገነን መሪ አለመሆናቸውን የሚያሳዩ ጥናቶች የሚሰሩበት የጥናት ማዕከል በስማቸው ለመክፈት ማቀዱን አስታወቀ፡፡
ፓርቲው 2016ን የስታሊን አመት በሚል ለማክበር ማቀዱን እንዳስታወቀ የዘገበው ቢቢሲ፣ አመቱን ሙሉ የሚከናወኑ የተለያዩ ስታሊንን የሚዘክሩ ዝግጅቶችን ለማሳካት እየተንቀሳቀሱ እንደሚገኙና በስታሊን ስም ሊቋቋም የታሰበው የጥናት ማዕከልም ሰውዬውን በአምባገነንነት በመወንጀል ያለ አግባብ ስማቸውን የሚያጠፉ አካላትን ፕሮፓጋንዳ የሚያከሽፉ ፊልሞች እንደሚታዩበት የፓርቲው ሃላፊ ጂኦርጂ ካሜኔቭ መናገራቸውን ገልጧል፡፡
የስታሊን አመት ክብረ በዓል ከሁለት ሳምንታት በፊት በሚከፈት የፎቶ ግራፍ ኢግዚቢሽንና የስታሊን የልደት በዓል ስነስርአት የሚጀመር እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ በመጋቢት ወር መጀመሪያም ስታሊን የሞተበት ዕለት በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚከበር አስታውቋል፡፡
መጪው የፈረንጆች አዲስ አመት የስታሊን ህገ መንግስት በመባል የሚታወቀው የሩስያ ህገ መንግስት የጸደቀበት 80ኛ አመት መሆኑን ያስታወሰው ዘገባው፣ ኮሙኒስት ፓርቲውም በስታሊን ታላቅነት ዙሪያ ምርምር ለሚያደርጉ ወጣት ተመራማሪዎች የገንዘብ ድጋፍ ለማድረግ ማቀዱን አመልክቷል፡፡

     በሪል ኢስቴትና በኮንስትራክሽን ግብአቶች ላይ ያተኮረ ዓለም አቀፍ ኤግዚቢሽን ለሦስት ቀናት ሊካሄድ ነው፡፡
አጀት ፕሮሞሽን ከመከር ሪል ስቴት ጋር በመተባበር ያዘጋጀውና Home up የተሰኘው ይኸው ኤግዚቢሽን፣ በኮንስትራክሽኑ ዘርፍ የተሰማሩ አካላትን እርስ በርስ ለማገናኘትና የገበያ ትስስርን እንዲፈጥሩ ለማድረግ ከማስቻሉም በላይ ልምድና ተሞክሮአቸውን እንዲለዋወጡ እንዲሁም ከአዳዲስ ቴክኖሎጂዎች ጋር እንዲተዋወቁ በማድረግ በከተሞች ውስጥ የሚታየውን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመቅረፍ ጥረግ በማድረግ ላይ የሚገኙትን የዘርፉን አካላት እንደሚያግዝ ተገልጿል፡፡
በሀርመኒ ሆቴል በተዘጋጀ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ኤግዚቢሽኑ የግሉን ዘርፍ ከመንግስት አካላት ጋር በማገናኘትና በማወያየት በዘርፉ የሚታዩ ችግሮችን ለማስወገድ እንደሚረዳ የጠቆሙት የአጀት ፕሮሞሽን ዋና ሥራ አስኪያጅ ወ/ሪት ኤልሳቤጥ አድነው፣ ከዚህ በተጨማሪም በኮንስትራክሽኑ ዘርፍ እየታየ ያለውን የመረጃ ክፍተት በመሙላት ኢንዱስትሪው አድጎ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እንዲሆን ያግዛል ብለዋል፡፡
በኤግዚቢሽኑ የአገር ውስጥና የውጭ አገር የሪል ኢስቴት አልሚዎች፣ የኪንስትራክሽን ግብዓት አቅራቢዎች፣ ፈርኒቸር አምራቾችና የፋይናንስ ተቋማት ተሳታፊ እንደሚሆኑም ተገልጿል፡፡ 

    በቴዎድሮስ በየነ የተዘጋጀው “ህብረ ኢትዮጵያ” የተሰኘ የጠቅላላ እውቀት መፅሀፍ ሰሞኑን በገበያ ላይ ዋለ፡፡ መጽሐፉ ስለኢትዮጵያ ታሪክ፣ ባህል፣ ስፖርት፣ ቱሪዝምና በአጠቃላይ ከ20ሺህ በላይ መረጃዎችን ያከተተ ሲሆን በየትኛውም የእውቀት ደረጃ ላይ ለሚገኝ፣ ማንኛውም አይነት ሰው፣ ያሻውን መረጃ ለማግኘት እንደሚረዳ ተገልጿል፡፡ በ328 ገፆች ተቀንብቦ የተሰናዳው ይህ መጽሐፍ፤ በ69 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

    ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ የመፅሐፍ ንባብ ፕሮግራም ከኢትዮጵስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር በነገው ዕለት ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ “ሰልፍ ሜዳ” በተሰኘው የደራሲ የግርማ ተስፋው መፅሀፍ ዙሪያ ውይይት ያካሂዳል፡፡ በወመዘክር አዳራሽ ለሚካሄደው ለዚህ ውይይት የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት አቶ ስለሺ ሀጎስ ሲሆኑ፤ የመፃሕፍት አፍቃሪያን በውይይቱ ላይ እንዲሳተፉ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ጋብዟል፡፡

Saturday, 12 December 2015 11:30

የኪነት ጥግ

(ስለ ልምምድ)
በልምምድ ወቅት ስህተቶችን መስራት አለብህ፡፡ ምክንያቱም እንደዚያ ነው የሚሆነውንና የማይሆነውን የምታውቀው፡፡
ክላርክ ፒተርስ
እውነት ብዙ ልምምድ አይፈልግም፡፡
ባርባራ ኪንግሶልቨር
ሦስት ሴት ልጆች አሉኝ፤ እናም ውጤቱ “ኪንግ ሊር”ን ያለ ልምምድ መተወን ሆነ፡፡
ፒተር ኢስቲኖቭ
በአንድ ወቅት በአራት ቀን ልምምድ ለአንድ ትወና መድረክ ላይ ወጥቼ ነበር፡፡
አና ፍሪል
እኔ የ6 ሳምንት የልምምድ ጊዜ ያስፈልገኛል፤ ሴቶች ደግሞ 9 ወራት ያስፈልጋቸዋል፤ ይሄንን ለመገንዘብ 15 ዓመት ፈጅቶብኛል፡፡
ዊሊያም ኸርት
ከመድረክ ይልቅ ፊልምን እመርጣለሁ። ሁልጊዜም ከትወናው በተሻለ ልምምዱን እወደዋለሁ፡፡
ብራድ ዶሪፍ
የልምምድ ሂደቱን ከልቤ እወደዋለሁ፡፡ እነዚያን በቀን 8 ሰዓት የልምምድ ጊዜያት! ተዋናዮችን በእጅጉ ነው የምወዳቸው፡፡
ፐርል ክሊጅ
ምንጊዜም በልምምድ ክፍል ውስጥ ስሆን ደስተኛ ነኝ፡፡ እዚያ ነው ሁልጊዜ ሙሉ አቅሜንና የፈጠራ ችሎታዬን የማገኘው፡፡
ሎውሪ ሜትካልፍ
አንድ ጊዜ ልምምድ ውስጥ ከገባህ በኋላ በክፍሉ ውስጥ ባለው ትርኢት ላይ ማተኮር አለብህ ብዬ አስባለሁ፡፡
ስኮት ኢሊስ
የሻወር ትዕይንት ከመስራት የበለጠ ገልጃጃ ነገር ምን አለ? የሻወር ትዕይንትን ለማለማ መድ፡፡
ኮቢ ስሙልደርስ
ቲያትርን መለማመድ  ለቃለ - ተውኔቱ ስጋ ማልበስ ነው፡፡ ተውኔትን ማሳተም ሂደቱን መገልበጥ ነው፡፡
ፒተር ሻፌር
በቲያትር ልምምድ ወቅት ትኩረቴን በሂደት ላይ ካለው ሥራ ሊያናጥበኝ ከሚችል ምንም  ዓይነት ንባብ ለመታቀብ እጥራለሁ፡፡
ሜርሴዲስ ማክካምብሪጅ

Saturday, 12 December 2015 11:28

የግጥም ጥግ

እዬዬ ማይገልፀው
ምን ይበል አባቷ
ምን ትበል እናቱ
ለወግ ያሰበችው ሲቀጠፍ በከንቱ
ምን ይላል ወገኔ
ጉንጬ በእምባ ሲርስ - አንጀቴ ሲታጠፍ
ኮትኩቼ ያበበው
መዐዛው ሚስበው
የማታ አበባዬ በአጭሩ ሲቀጠፍ
ያቺ ምስኪን እናት
የማታዋን ሳታውቅ በጠዋት ተነስታ
ከዛሬው ወጋገን የነገውን አይታ
ጨርሳ አትሸኘው
ለአይኗ እንኳ ሳስታ
በደንብ እንዳትስመው
ያንን ስርጉድ ጉንጩን
ብሉኝ ብሉኝ ሚለው
ሞልቶ-ትርፍ ፈገግታ
የጠዋት ፀሎቷ - ጅምር በረከቷ - በእንባዋ
 ሲታበስ
የፀበል ማቆርያ - የህመም
ብርታቷ - ሲሰበር ላይታፈስ
እንዴት አሟት ይሆን
ልቧ ውስጧ ሲሞት
ያልጠና አጥንቱ - ያልገራ ጅማቱ - ጎማ
ሲበትነው
ያልቦረቀች ነፍሱ - ጅምር ለጋነቱ - ሲቃ
ሲፈትነው
እህህ አይገልፀው
እዬዬ አይክሰው
እምባዋን ረጭታው -
ከመብሰክሰክ በቀር - ምን ታደርገዋች
አንዴ ፈሷል ነገር - ዳግመኛ አትወልደው -
በምን ታፍሰዋለች
(መታሰቢያነቱ ሰሞኑን በአዲስ አበባ ከትምህርት ቤት ሲመለሱ በመኪና አደጋ ህይወታቸውን ላጡት ህጻናት ይሁንልኝ፡፡)
(ከዘም ዛሚ ፌስቡክ)