Administrator

Administrator

    ለ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና መቋረጥ ምክንያት የሆነውን የፈተና መሰረቅ ጉዳይ ፖሊስ እየመረመረ መሆኑ የተገለፀ ሲሆን ለድጋሚ ፈተና የህትመትና የመጠረዝ ስራ እየተከናወነ ነው ተብሏል፡፡
በስርቆቱ ጉዳይ የሚደረገው ምርመራ በተጠናከረ መልኩ ሙሉ ለሙሉ በፀጥታ ኃይሎች መያዙን ያስታወቁት በትምህርት ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አህመድ ሲራጅ፤ ጉዳዩን ተከታትሎ ለህግ የማቅረብ ስራ የፖሊስ መሆኑን ጠቁመው ጉዳዩ የፀጥታ አካላት የሚፈትኑበት ነው ብለዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ አዲስ አድማስ ያነጋገራቸው የህግ ባለሙያ፤ በመንግስት ከፍተኛ መስሪያ ቤት እንዲህ ያለው ወንጀል ሲያጋጥም ፖሊስ በሁለት መንገድ ምርጫ ሊያደርግ እንደሚችል ጠቅሰው አንደኛ ቀጥታ ጥቆማ ከመስሪያ ቤቱ ሲደርሰው፣ ጥቆማ ካልደረሰው ያገኘውን ፍንጭ መነሻ አድርጎ ምርመራ እንደሚያደርግ አብራርተው፤ ማህበራዊ ድረ ገፅ ላይ “ፈተናው ተሰርቋል” ተብሎ ይፋ በተደረገ ጊዜ ፖሊስ ምን ህል ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ ምርመራ ለማድረግ እንደሞከረ መጠየቅ አለበት ብለዋል፡፡ ትምሀርት ሚኒስቴር በበኩሉ፤ በአሁን ወቅት በዋናነት ትኩረት የሰጠው ፈተናው በድጋሚ በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ በጥንቃቄ ማካሄድ በሚቻልበት ጉዳይ ላይ መሆኑን የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
ቀደም ሲል ፈተናው ተጠርዞ፣ ታሽጎ፣ በሀገሪቱ በሚገኙ 802 የፈተና ጣቢያዎችና በውጭ ሀገር በሚገኙ 3 ጣቢያዎች ለማድረስ እስከ 3 ወር ይፈጅ እንደነበርና የተዘጋጀው መጠባበቂያ ፈተና በልዩ ግብረ ኃይል እየተመራ፣ ከፍተኛ ርብርብ በማድረግ በ23 ቀን ውስጥ ሁሉንም ጉዳዮች ለማጠናቀቅ ጥረት እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡
ፈተናውን ለመስጠት የታቀደው ከሰኔ 22 እስከ 30 ባለው ጊዜ ውስጥ ሲሆን የረመዳን የፆም ወቅት መሆኑንና የኢድአል ፈጥር በአልም ከተያዙት ቀናት መካከል በአንዱ ሊሆን እንደሚችል በመግለፅ የተያዘው ፕሮግራም እንዲቀየር እየተጠየቀ ቢሆንም ትምህርት ሚኒስቴር ፕሮግራሙን እንደማይቀይር አስታውቋል፡፡
ፈተናው ተሰርቆ መውጣቱ ተረጋግጦ ቀደም ያለው መርሃ ግብር ከተሰረዘ በኋላ በአጭር ጊዜ ውስጥ ፈተናውን እንዴት መስጠት ይቻላል በሚለው ላይ አመራሮችና ባለሙያዎች ውይይት ማድረጋቸውን ሃላፊው ጠቁመው፤ በ23 ቀናት ውስጥ ማከናወን እንደሚቻል ታምኖበት ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴ መገባቱን ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል ይሄም የተማሪዎችን የጭንቀትና የመቆዘሚያ ጊዜ ለመቀነስ ታስቦ ነው” ገልፀዋል - ይሄም፡፡
የረመዳን ወር መሆኑ እንደሚታወቅና ካለው ችግር አንፃር በአሉ የሚውልበትን ቀን መዝለሉ አማራጭ ሆኖ መገኘቱን ያብራሩት ኃላፊው የረመዳንን ወር “ፆም ከስራ ጋር የታረቀ  ህብረተሰብ በስራ የሚያሳልፈው መሆኑን ሙስሊሙ ህብረተሰብም መንግስት ያለበትን ጫና በአግባቡ ይረዳል የሚል እምነት እንዳለ ተናግረዋል፡፡ አሁን በድጋሚ ከተያዘው ቀን ወደፊት ይራዘም ቢባል የፈተና ማረሚያ፣ ውጤት ማሳወቂያና የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ፕሮግራሞችን የሚያፋልስ መሆኑን ያስረዱት ኃላፊው አስቀድሞ የተያዘውን የጊዜ ሰሌዳ ለማሳካት ሲባል ርብርብ ማድረጉ አስፈላጊ ሆኗል ብለዋል፡፡

     የኦስካር ተሸላሚዋ የፊልም ተዋናይት አንጀሊና ጆሊ በታዋቂው የለንደን ስኩል ኦፍ ኢኮኖሚክስ በቀጣዩ አመት በሚጀመረው የሁለተኛ ዲግሪ ፕሮግራም የሴቶች፣ የሰላምና የደህንነት ኮርስ ተጋባዥ መምህርት ሆና ለማስተማር መመረጧን ዩኒቨርሲቲው አስታወቀ፡፡የፊልም ተዋናይቷ ከታዋቂዎቹ የእንግሊዝ ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ በሆነው የለንደን ስኩል ኦፍ ኢኮኖሚክስ ከሴቶች፣ ከሰላም፣ ከደህንነት፣ ከሰብዓዊ መብቶችና ከጾታ ጋር የተገናኙ ጉዳዮችን ከማስተማር በተጨማሪ፣ በተለያዩ ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ንግግር እንደምታደርግ፣በአውደጥናቶችና በህዝባዊ ዝግጅቶች ላይም እንደምትሳተፍ ታውቋል፡፡
 “ተማሪዎችን ለማስተማርና ከእነሱም ለመማር ጓጉቻለሁ” ያለቺው አንጀሊና ጆሊ፣ከተማሪዎቿ ጋር ልምዶችን እንደምትለዋወጥና በጉዳዩ ዙሪያ ከተለያዩ የአለማችን አገራት መንግስታትና ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጋር በትብብር እንደምትሰራም ገልጻለች፡፡
አንጀሊና ጆሊ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ተቋም የበጎ ምግባር አምባሳደርና ልዩ መልዕክተኛ ከመሆኗ በተጨማሪ በአለማቀፍ ደረጃ በሚከናወኑ የሴቶች የመብት ጥሰቶች፣ ጾታዊ ጥቃቶች፣ የህጻናት ደህንነት እንክብካቤዎችና በሌሎች የበጎ ምግባር እንቅስቃሴዎች ላይ በመሳተፍ ትታወቃለች፡፡

Monday, 30 May 2016 09:22

የፍትሕ ኤልኒኖ!

   ከብዙ የሃሳብ መንሸራሸር በኋላ የቢሮ ኃላፊው ጠንከር ያለ አስተያየት ሰጡ፡፡ ‹‹ታውቃላችሁ? እኛ የምንነጋገረው የቢሮአችንን፣ የአገራችንን እንዲሁም የመንግስታችንን ጥቅም በሚያስከብር ጉዳይ ነው፡፡ በእርግጠኝነት ይህቺ ሴት ለዚህ ቢሮም ሆነ ለአገራችን  እድገትና ትራንስፎርሜሽን የማታስፈልግ ናት ብል ማጋነን አይሆንብኝም፡፡ እሷ እኮ ሌላው ቢቀር ለመንግስት ፖሊሲና ስትራቴጂ እንኳን ደንታ የሌላት፣ የአመለካከት ችግር ያለባትና ልማት አደናቃፊ ሴት ነች›› አሉ፡፡
ለዛሬው የጭንቅ አጀንዳቸው መንስኤዋ ኤፍራታ ይመር ናት፡፡ ኤፍራታ ቀውላላ ቁመት፣ ረጂም ጸጉር፣ ንጹህ ልብ፣ ብሩህ አዕምሮ የታደለች የ31 ዓመት ልጅ እግር ናት፡፡ እልኸኛ ከመሆኗ በተጨማሪ መበለጥን አብዝታ ትጠላለች፡፡ ተማሪ እያለች የምትናደደው በመሳሳቷ ሳይሆን በሌላ ተማሪ ከተበለጠች ነበር፡፡ ብዙ ማውራትም ሆነ ከወንዶች ጋር መቀለድ አትፈልግም፡፡ ከባሏም ጋር የተፋታችበት ምክንያት አቋም የሌለውና ልክስክስ መሆኑን በመረጃ ከደረሰችበት በኋላ ነበር፡፡ ትክክል አለመሆኑን ብታውቅም የስልክ ጥሪዎችን በመቅረጽም ሆነ ሰነዶችን ‹‹ኮፒ›› በማድረግ ማንም አይደርስባትም፡፡፡ የዛሬን ፍቅር ሳይሆን የነገን ማሰብ ይበጃል ትላለች፡፡ ሲበዛ ጠንቃቃና ለቃሏ ታማኝ ነች፡፡ ‹‹ክርስቶስን አደርገዋለሁ!›› ብላ የማለችበትን ነገር ሳታደርግ አታፈገፍግም፡፡
የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተሩ ኤልያስ፤ቦርጩን እያሻሸ  ራሱን ከፍ ዝቅ በማድረግ በአድናቆት ጭምር የሀሳቡን ትክክለኝነት አረጋገጠ፡፡ የቢሮ ኃላፊው የሁሉንም ስሜት ለመረዳት ወደ ሌሎቹ አማተረ፡፡
የፋይናንስ አስተዳደሩም፤‹‹ልክ ነው›› ለማለት ራሱን ነቀነቀ፡፡ የግዢ አስተዳደሩ ጉሮሮውን ጠራርጎ፣ተንኮለኛ ዓይኑን እያጉረጠረጠ፤‹‹ልክ ነው›› አለ፡፡ ‹‹ግን ሴትዮዋ አደገኛ ናት፡፡ የሆነ ነገር ካልተደረገች ሌላ መዘዝ ማምጣቷ አይቀርም፡፡ መቼም ድርቅናዋንና ሐቀኝነቷን ሁላችንም እናውቀዋለን›› ብሎ ማብራራት ከጀመረ በኋላ፣ደጋፊዋ ነህ እንዳይባል ስለሰጋ መልሶ ተወው፡፡
የቢሮ ኃላፊው ቀብረር ብሎ፤‹‹ምንም አታመጣም አትስጉ፡፡ አሁን በተወያየንበት ጉዳይ  ከተስማማን፣ በተነጋገርነው መሰረት ቃለ-ጉባዔውን እንፈራረምበት፡፡ ከዚያም በኋላ በራሷ ወጥመድ ስትታነቅ ሁሉም ነገር ይገባታል፡፡ አይደለም ውሰጂ የተባለችውን ሲሳይ ይቅርና ኪስ ማውለቅ ትጀምራለች፡፡›› አለ የምጸት ሳቅ እየሳቀ፡፡ እነሱም አብረው ሳቁ፡፡
የቢሮ ኃላፊው ሲያወራ  ባያስቅም መሳቅ፣ ሳይገባቸው  የገባቸው ለመምሰል ራሳቸውን መነቅነቅ የዘወትር ተግባራቸው ነው፡፡
      የቢሮ ኃላፊው የፖለቲካ ሹም ከመሆኑም ባሻገር ብዙ ገንዘብ የሰበሰበ በመሆኑ በቅርበት የሚያውቁት ‹‹እጁ ረጂም ነው›› ይሉታል፡፡
 በየትኛውም መንገድ ቢመጡበት መውጫ ቀዳዳ አለማጣቱ ብቻ ሳይሆን ነገር አዋቂና የፈለገውን መጥቀም፣ የፈለገውን መጉዳት የሚችል ሰው በመሆኑ ጭምር ነው፡፡ ሌላው ልዩ የሚያደርገው ነገር በሚሊዮን ብር እያፈሰ በአካውንቱ ውስጥ እዚህ ግባ የሚባል ብር አለመገኘቱ ነው፡፡ በየትኛው አካውንት የትኛው ባንክ ያስገባው ወይም ቆፍሮ ይቅበረው፣ በውጪ ዓለም ባሉ ባንኮች ያሽሸው እስካሁን የሚታወቅ ምስጢር የለም፡፡
     ጉቦ ሲቀበልም በጣም ጠንቃቃ ከመሆኑ የተነሳ፣ የሚቀበለው በጥሬ ብር በሚያምነው ሰው አማካኝነት  ብቻ ነው፡፡ አለዚያም ለሆነ ሰው፣ በሆነ ስም፣ ከሆነ ሰው፣ ወደሆነ ሰው፣ ለሌላ ሰው፣ በሌላ ሰው ስም ይደርሰዋል እንጂ በቼክ ወይም በአካውንቱ ብር ፈጽሞ አይቀበልም፡፡
በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠር ብር የሚፈርምበት አጋጣሚ ካለ፣ ስብሰባ ወይም ሌላ ምክንያት ፈጥሮ ወክሎ ይጠፋል፡፡ ሁሉንም ነገር በስልክ በወከለው ሰው አማካኝነት ‹‹ፈርምላቸው፤እንዲህ አድርገው…›› እያለ  በማስፈጸም ራሱን ነጻ ለማድረግ ሁሌም የተዘጋጀ  ክፉ ሰው ነው፡፡ ትልቁ  ብልጠቱ ደግሞ የሚገባውን ነገር ለሚገባው ሰው አለመንፈጉ ነው፡፡ አብዛኛው ሰው የሚያደንቀው ግን ሁሉንም ቤተሰቦቹን ከድህነት አረንቋ ማውጣት የቻለ ጀግና በመሆኑ ነው፡፡ ዘመድ ቤተሰቡ ይቅርና ሰፈርተኛውም እንደ ዓይናቸው ብሌን ይጠነቀቁለታል፡፡ ተቸገርኩ ብሎ የመጣን ሰው አይመልስም፡፡ ማንን ይዞ ከማን ጋር መሥራት እንዳለበት ጠንቅቆ የሚያውቅ መሰሪ ነው፡፡  አሁን አሁንማ ሰዎች አሰራሩን ከእሱ የበለጠ የተረዱት ይመስላሉ፡፡
   ሁሉም የሥራ ኃላፊዎች ሀሳብ ከመስጠት ይልቅ የእሱን ሀሳብ በማድነቅ እንደ ወትሮው አጸደቁ፡፡ ቃለ ጉባዔውን እየተፈራረሙ ሳለ ምንም ሀሳብ ያልሰነዘረው፣ በዝምታው የሚታወቀው የሰው ኃይል አስተዳደሩ ዳውድ፤ ‹‹እእህ…›› አለ፡፡ የቢሮ ኃላፊው ስለሚረዳው እንጂ የተናገረ ሳይሆን ሽንት ቤት ሆኖ፣ “ሰው አለ” ያለ ነበር የሚመስለው፡፡
‹‹የምትጨምረው ሀሳብ አለህ እንዴ ዳውድ?›› አለው የቢሮ ኃላፊው፡፡ ዳውድም ምንም የገጽታ ለውጥ በፊቱ ሳይታይ፤‹‹ያው አሁን በተነጋገርነው በሁሉም ነገር እስማማለሁ፤ እፈርማለሁም፡፡  ነገር ግን እርሷ ቀድማ የሥራ መልቀቂያ አስገብታለች›› አለ፡፡
     የቢሮ ኃላፊው መብረቅ የመታው ያክል ደርቆ ቀረ፡፡ ሌሎቹም ንስር እንደወሰዳት ጫጩት ነፍሳቸው ለሰከንዶች ቀጥ አለ፡፡ ሁሉም ክው አሉ፡፡ እንደገና ተያዩ፡፡ እስካሁን ስላልነገራቸው ተናደዱ፡፡ ነገር ግን የእሱን ባህርይ አብጠርጥረው ስለሚያውቁ ለምን እስካሁን አልነገርከንም በማለት ጊዜያቸውን ማጥፋት አልፈለጉም፡፡ ከዚህ በፊት ብዙ  ነገርን ታቅፎ ሳይነግራቸው  በመቅረቱ ተጨቃጭቀዋል፡፡ ብዙ ጥቅማ ጥቅምም ማግኘት እያለበት ትተውታል፡፡ አይታረምም እንጂ ማስጠንቀቂያ ደብዳቤም በተደጋጋሚ ተጽፎበታል፡፡ የሚገርመው ግን እስካሁን ማስጠንቀቂያ ደብዳቤዎቹ ምን እንደሚሉ አላነበባቸውም፡፡ የሚሰበሰበው ግዴታው ስለሆነ እንጂ ምንም ሳይናገር ስብሰባው የሚዘጋበት ጊዜ ብዙ ነው፡፡
‹‹እንዴት ሆኖ?›› አለ የቢሮ ኃላፊው፤ሁሉንም በአንዴ ለማየት እየሞከረ፤‹‹እኔ መጀመሪያም ያልኩት ይሄን ነው፡፡ ልትቀድመን አስባለች ማለት ነው›› አለ የግዢ አስተዳደሩ፡፡  
ሁሉም ሲደናገጡ ዳውድ ተረጋግቶ የሚሆነውን ይመለከታል፡፡ የሰው ኃይል አስተዳደር በመሆኑ ብዙ ነገሮች ይገጥሙታል፡፡ ነገር ግን ሁሉንም በንቀት ‹‹ከንቱ›› በማለት ያልፈዋል፡፡ በግዴለሽነት ብዙ ነገርን አሳልፏል፡፡ ምንም ይሁን ምን፣ ማንም ይሁን ማንም፣ ምንም አይመስለውም፡፡ ‹‹አይ አላህ ተው ሰውን ክፉ አታድርገው›› ይላል አንዳንድ ጊዜ ሲመረቅን፡፡ ሥራ ሆኖበት እንጂ ከጫት ውጪ ከማንም ጋር ባያወራ ደስታውን አይችለውም፡፡ ለመማርም ሆነ ራሱን ለማሻሻል እንደ ሌሎቹ አይሯሯጥም፡፡ የቢሮ ኃላፊው ብዙ ስለማይጨቀጭቀው ብቻም ሳይሆን ቢቆፍሩትም ምስጢር ባለማውጣቱ ይደነቅበታል፡፡ የማንንም ቢሆን ለማንም አያወራም፡፡ አንዳንድ ጊዜ ሲያጋንኑለት፤‹‹የሰማውን ወሬ ለሰው ሊያወራ ቀርቶ ለራሱም ደግሞ አይናገርም›› ይሉታል፡፡ በእርግጥም እሱ ካለበት ሳይነቃነቅ ብዙ ኃላፊዎች ተቀያይረዋል፡፡ ስላለፉትም ሆነ አሁን ስላሉት የሚናገረው ስማቸውን ብቻ ነው፡፡
ካልቀጠርከኝ ብለው ከሚጣሉት ሰዎች በተጨማሪ የበላይ ኃላፊዎችና ዳይሬክተሮቹ ዘመዳቸውን እያመጡ ቅጠርልን ስለሚሉት አንጀቱ ብግን፤ድብን ይላል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ይህን ሥራ ለቆ ለመሄድ ቢያስብም ሁሉም ቦታ ያው መሆኑን በመረዳቱ እየተጎዳ ይኖራል፡፡ ‹‹ሰው ክፉ›› ይላል  በዝምታው መሀል፡፡ መርቀን ብሎ ለሚወዳቸው እንደሚናገረው ከሆነ፣ ሁሉም መስሪያ ቤቶች በዚህ ጉዳይ አንድ ዓይነት ናቸው፡፡ አንዳንዱ በብሔር፣ አንዳንዱ በሀይማኖት፣ አንዳንዱ በጎሳ፣ አንዳንዱ በገንዘብ አለዚያም ጾታዊ ግንኙነት በማድረግ ቅጥር ይፈጸማል፡፡ ዳውድን የሚያናድደው ነገር ውድድር የሚባለው ከንቱ ልፋት ነው፡፡ ምንም እንኳን እሱም በሕጉ መሰረት ባይሰራም፣ ሁሌም ከራሱ ጋር እንደተካሰሰና እንደተዋቀሰ ይኖራል፡፡ ስንት የድሃ ልጅ እውቀቱን ተማምኖ፣ ስንት አገር አቋርጦ፣ ስንት ፍዳ ቀምሶ፣ ተቸግሮ፣ እየተራበ፣ ያልፍልኛል ብሎ እየተንከራተተ፣ ለይምሰል ማወዳደሩ በጣም ያናድደዋል፡፡ እንደውም ዳውድ በውድድር ጊዜ ከሩቅ አገር ያመለከቱትን አይደውልላቸውም፡፡ በዚህም የተነሳ ተወዳዳሪዎቹ በዳውድ ላይ አንዳንዴ ቂም ይይዙበታል፡፡ እርሱ ግን ውስጡን ስለሚያውቅ እንዳይንከራተቱ  በማሰብ ነው፡፡  ዳውድ በትክክል ያለፈውን ሰው ትቶ፣ የቢሮ ኃላፊው ቅጠር ያለውን የሚቀጥርበት ጊዜ አለ፡፡ እንደውም ቅጥር ከተፈጸመ በኋላ ‹‹ለፎርማሊቲው ማስታወቂያ አውጣ›› የሚባልበት ጊዜ በጣም ብዙ ነው፡፡ ‹‹አይ አላህ ኧረ ተው ሰውን ክፉ አታድርገው›› ብሎ የታዘዘውን እየተቃጠለ ይፈጽማል፡፡ ማንም ግን ንዴቱን አያውቅበትም፡፡ ከአፉ ክፉ ቃል መናገርም ሆነ  ሰው በእሱ እንዲከፋ አይፈልግም፡፡
‹‹ታድያ ምን እናድርግ?›› አለ የቢሮ ኃላፊው፤ጭንቀቱ እንዳይታወቅበት እየጣረ፡፡
የህዝብ ግንኙነቱ ዳይሬክተሩ ኤልያስም፤‹‹የሆነ ምክንያት ተፈልጎ መታሰር ነው ያለባት፡፡ አለዚያ ሌላ ችግር ውስጥ ታስገባናለች፡፡ በተለይ የባለፈው ጨረታ ከተመረመረ ብዙ ችግሮች ይገኙብናል፡፡ ሁላችንም ሸቤ መግባታችን ነው›› ሸቤ የምትለዋን ቃል ከተናገረ በኋላ ከአፉ ስላመለጠችው ተጸጸተ፡፡ ግን ማናቸውም ቢሆኑ አጽንኦት አልሰጧትም፡፡ አሊያም አልገባቸውም ወይንም ደግሞ ቀድመው ተረድተውት ይሆናል፡፡
‹‹እንዴት? ምን ዓይነት ምክንያት እንፈልግላታለን?›› አለ የፋይናንስ ኃላፊው ከጭንቁ የሚገላገልበት ዘዴ ያገኘ ስለመሰለው አንገቱን አስግጎ፡፡
የግዢ ኃላፊው፤‹‹በእርግጥ ከፈለግን ማስወንጀያ አናጣም፡፡ እርሷ ተወክላ የፈረመቺበት ሰነድ ይኖራል፡፡ በዚያ ልናሳሥራት እንችላለን›› አለ፡፡
የፋይናንስ አስተዳደሩ እንደ መሳቅም እንደ መናደድም ብሎ፤ ‹‹እኔስ? ታዝዤ ነው የፈረምሁት ልበል? ወይስ ተሳስቼ ነው እንድል ትፈልጋለህ? ማንም ይፈርመው አግባብ ከሌለውና ችግር ካለበት እንደ ፋይናንስ አስተዳደርነቴ የማስቆም ኃላፊነት አለብኝ፡፡ እሱ ሌላ መዘዝ ነው፡፡ ሌላ መፍትሔ ካለህ ተናገር›› አለ በማያወላውል አቋም፡፡  
በሆነ ጊዜ የቢሮ ኃላፊው እየወከላት ብዙ ጊዜ ይጠፋ ነበር፡፡ በርከት ያለች ብር ከሆነች ስብሰባ፣ ስልጠና፣ መስክ እያለ በምክንያት  ወክሏት ይሰወር ነበር፡፡ ያኔም በስልክ ፈርሚላቸው ብሏት በስንት ጭቅጭቅ አሳምነዋት የፈረመቺው ሰነድ ስለነበር በዚያ ለመወንጀል ፈልገው ነበር፡፡ ያም ቢሆን እንዳማያዋጣቸው ተረድተዋል፡፡ ኤፍራታ መርዝ ስለሆነች መረጃ ይዛባቸው እንደሆነም ይጠራጠራሉ፡፡                  
የግዢ ኃላፊ፤‹‹ሌላ አማራጭ… አ…ለ! ለምን እንዳትሞት አድርገን በመኪና አናስገጫትም፡፡ ከዚያ እናሳክማታለን፣ እንከባከባታለን›› አለ፡፡
የሰው ኃይል አስተዳደሩ ዳውድ በድንገት፤‹‹ያረሱል አሚን ያለህ! ኧረ በጭራሽ ይህ የማይሆን ነው›› አለ፡፡ እንደ ዳውድ ሌሎቹም አይቃወሙ እንጂ ሁሉም ደግንጠዋል፡፡ ምክንያቱም እንደ እነሱ በሙስና አልጨማለቅም ማለቷ እንጂ ባህሪይዋን፣ መልካምነቷን፣ በሥራዋ ያላትን ታማኝነትና ጥንካሬ፣ ከሁሉም በላይ ለአመነችበት ነገር ያላትን ጽናትና ክብር የቢሮ ኃላፊው ጭምር ያደንቁላታል፡፡ ይወዱላታልም፡፡ ምን ይደረግ? ወይ አትበላ ወይ አታስበላ!   
     ‹‹እና ምን ይሁን? እንደማይመለከትህ እጅህን አጣጥፈህ ዝም ትላለህ እንዴ? አደጋ ውስጥ እንዳለን ታውቃለህ አይደል? ከርቸሌ ከገባን ሁላችንም እንደምንገባ እወቁ፡፡ የምንፈራረማቸው ቃለ-ጉባዔዎች እስካልተፈተሹ ጊዜ ድረስ ነው ህጋዊ ሆነው የሚቀጥሉት፡፡ ከተመረመሩ ግን…›› አለው በእሷ ቦታ የተወከለው ምክትል ቢሮ ኃላፊው ዳውድን በቁጣ፡፡ በእሷ ቦታ የተወከለው አስመሳይና ተሽቆጥቋጭ ስለሆነ ነው እየተባለ ይታማል፡፡ ‹
‹ማንን ታሸንፋለህ ሲባል፣ ወደ ሚስቱ ሮጠ›› እንዲሉ አበው መሆኑ ነው፣ ዳውድ ላይ መጮሁ፡፡ ይህቺ ሹመት ከተሰጠችው በኋላ ተራ ሰራተኞችን ማናገር እያንገሸገሸው ነው፡፡የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተሩ ኤልያስ፤‹‹ለምን እንዲህ አናደርግም፡፡ ሙስና አልበላም እያለች አይደል የምትመጻደቀው፣ የእኛ መዝገብ ቤቷ ልጅ ብድር አለብኝ ስትል ሰምቻለሁ፡፡ እዳሽን ክፈይ ብለን ልከናት ፎቶ እናነሳታለን፡፡ ከዚያም ፖሊሰ አሰማርተን ሙስና እየተቀበለች ነው ብለን ማሳሰር ነው፡፡ የመዝገብ ቤቷ ልጅ የተወሰነ ብር ከሰጠናት ለፍርድ ቤት ቃሏን እስከ መስጠት ትተባበረናለች፡፡ ምስክር ካስፈለገም ጓደኛዋን በገንዘብም፣በፍቅርም መቅረብ እንችላለን፡፡
ደመወዝ እንደሚጨመርለትና እድገት እንደሚሰጠው ተነግሮት፣በዚህ ኑሮ ውድነት እምቢ የሚል ሰራተኛ አይኖርም›› አለ ከሌሎቹ የተሻለ ብልህ ነኝ ብሎ ስለሚያስብ ዓይነ ዓይናቸውን እያየ፡፡ ሁሉም በየተራ  መፍትሄ የሚሉትን ሀሳብ አቀረቡ፡፡ በጸጥታ ሲከታተል የነበረው የቢሮ ኃላፊው ተናደደ፡፡ የአንዳቸውም ሃሳብ አላረካውም፡፡ ጉዳዩን ላያዳግም መቅበር ነው ፍላጎቱ፡፡ ‹‹ስንት አስቸጋሪና ውስብስብ ነገር እንዳላለፍን አንዲት እንከፍ ታስቸግረን!? በሽጉጥ  ነበር መድፋት፡፡ ብይ! ተጠቀሚ፣ ከሰው እኩል ሁኚ ስትባል እንቢ ትላለች? እሷ ብሎ የአገር ተቆርቋሪ፡፡ እንኳን እሷ ስንቶቹ የአገሪቱ ከፍተኛ ባለሥልጣንም ይመዘብራሉ፡፡
አዲስ ነገር ነው እንዴ? ቆይ አሳያታለሁ›› አለ ጠረጴዛውን በመደብደብ፡፡ ሲናደድ ግንባሩ ከመቆጣጠሩና ላቡ ግጥም ከማለቱ በላይ ዓይኑ በክፋት የተሞላች የተኩላ ዓይን ትመስላለች፡፡
     የቢሮ ኃላፊው፤‹‹በቃ ሁሉንም ለኔ ተውት›› ብሎ የስልኩን እጀታ አነሳ፡፡ ‹‹ዳውድ እቤቷ ወስደህ የምታስቀምጥልኝ ነገር አለ፡፡ ኤልያስ የባለፈውን ሰነድ እንድታመጣልኝ፡፡ አንተ ደግሞ ሰሞኑን ከእሷ ጋር ስለሚውለው ሰው ማንነት ሙሉ መረጃ እንድትነግረኝ እፈልጋለሁ፡፡
አንተኛው ፋይሎቹን በሙሉ ‹‹ኮፒ›› አድርግና በተነጋገርነው መሰረት እንደገና ሥራቸው፡፡ ሁላችሁም ተዘጋጁ፤የምነግራችሁንና የማዛችሁን ሰከንድ ሳታባክኑ፣ ሳትጠራጠሩ ማድረግ ነው፡፡ ምንም አታስቡ፤ስልጣኔን በአግባቡ የምጠቀምበት ሰዓት ይህ ነው›› አለ፡፡  ከዚያም በውል ወደሚያውቁት የደህንነት ሰው ጋ ስልክ ደውሎ፤ ስለ አክራሪነት፣ ሽብርተኝነትና ልማት አደናቃፊዎች ጥቂት ካወራ በኋላ በቢሮአቸው ውስጥ ስለተከሰተው ነገር ተገናኝተው ዝርዝሩን ማውራት እንዳለባቸው ተነጋግሮ ስልኩን ዘጋ፡፡ ሁሉም ተደናገጡ፡፡ አብዛኛዎቹ ነገሩ ወደ ሌላ እየተቀየረ መሆኑ ገባቸው፡፡
እውነትም እጀ ረጂም!! ‹‹እኔ የማደርገውን አሳያችኋለሁ፡፡ እድሜ ልኳን ትበሰብሳታለች፡፡
ሁላችሁም ለተልእኮው ተዘጋጁ፡፡ አንተ እንከፍ ደግሞ ስልክህን እንዳታጠፋ›› ብሎ  ምክትል ቢሮ ኃላፊውን ገላምጦት፣ ከእጁ የማትለየውን ጥቁር ቦርሳ አንጠልጥሎ ጥሎአቸው ወጣ፡፡ ሁሉም  ቆሌያቸው ተገፎ በዓይናቸው ሸኙት፡፡ ማንም ምንም ያለ አልነበረም፡፡ ጉዳዩ ከባድና የሁላቸውም እጅ እንደሚኖርበት ተገንዝበዋል፡፡ የቢሮ ኃላፊው ሁሉንም በማነካካት ለዘላለም በደም ተሳስረው እንዲኖሩ ማድረግን ያውቅበታል፡፡
 ማንም ከደሙ ንጹህ ነኝ ማለት አይችልም፡፡ ወደ ኋላ የሚያፈገግፍ ቢኖር የእሷ እጣ ፋንታ እንደሚደርስበትም አላጡትም፡፡ ዳውድ እንደ መሳቅ ብሎ የመጀመሪያው መልእክተኛ በመሆኑ እየተገረመ፤‹‹አሁን ከእኛ በላይ ልማት አደናቃፊ አለ!›› ሲል በምጸት ተናገረ፡፡
ከእርሱ በቀር ሁሉም ደንግጠው ስለነበረ የመለሰለት አልነበረም፡፡ ግዴለሽነቱ ከጭንቀት ቢያድነውም፣ከዚህ መ/ቤት በጊዜ ባለመልቀቁ መቆጨቱ አልቀረም፡፡
ሁሉም በየራሳቸው ዓለም በተቀመጡበት በሀሳብ ሰመጡ፡፡ “ዋ! ለኔ ….. ዋ! ለኔ…” የሚሉ ነፍሶች ተበራከቱ፡፡ ዳውድ ግን አሁን ወንድ መሆን እንዳለበት፤እንደተጫወቱበት የሚጫወትባቸው ጊዜ እንደደረሰ አሰበ፡፡ ‹‹ተጀመረ…!›› አለና በንቀት አይቷቸው፣እሱም ከቢሮው ወጣ፡፡ በድርቅ የተመታው የቢሮአቸው የፍትህ ኤልኒኖ፣ መከላከያው በእጆቹ ውስጥ ባሉት ዶሴዎች እንደሆነ እርግጠኛ ነበር፡፡  





    በአመልማል ደምሰው የተደረሰውና በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተው “ያልተቋጨ ጉዞ” የተሰኘ ልብ ወለድ መፅሀፍ የፊታችን አርብ ከቀኑ 11፡30 ሰዓት ጀምሮ በዋቢ ሸበሌ ሆቴል ይመረቃል፡፡ መቼቱን ጎንደር፣ ኤርትራ (አስመራ) አዲስ አበባ፣ ጅማና አሜሪካ ያደረገው ልብወለዱ፤ ልጅነትና ፍቅር ያላቸው ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ትስስር በውብ ቋንቋ ተገልፆበታል ተብሏል፡ ፡ በምርቃት ስነ - ስርዓቱ ላይ ደራሲያንና ገጣሚያን ስራዎቻቸውን እንደሚያቀርቡም ታውቋል፡፡ በ387 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ በ80 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

    ወደ እስራኤል አገር ለስራ ተጉዛ በመኖሪያ ፈቃድ እጦት ለእስር በተዳረገችው አብነት ከበደ የተፃፉ ወጐችና ግጥሞችን ያካተተው “በኖት በህደሪም” የተሰኘው መድበል ሰሞኑን ገበያ ላይ ዋለ፡፡ ፀሐፊዋ በእስራኤል አገር የመኖሪያ ፈቃድ ሳትይዝ በመገኘቷ ከመንገድ ላይ ተይዛ ከርቸሌ የተወረወረች ሲሆን በሁለት ዓመታት የእስር ቆይታዋ ያሳለፈችውን መከራ በወቅቱ ከእነስሜቷ በሁለት ወጐችና በበርካታ ግጥሞች ከትባዋለች ተብሏል፡፡ መጽሐፉ ባለፈው ሳምንት የተመረቀ ሲሆን በ45 ብር እንደሚሸጥ ታውቋል፡፡

በቀድሞው የቢቢሲ ጋዜጠኛ ኪት ባወርስ ተጽፎ በሻማ ቡክስ የታተመው “Imperial Exile” የተሰኘ መፅሐፍ ትላንት ምሽት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ተፈሪ መኮንን አዳራሽተመረቀ፡፡ መጽሐፉ በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተዘጋጀ ሲሆን ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ከ1936-40በእንግሊዝ አገር ያሳለፉትን የስደት ህይወት እንዲሁም ወደ አገራቸው የተመለሱበትን ሁኔታያስቃኛል ተብሏል፡፡ በ260 ገፆች የተሰናዳው መጽሐፉ፤በ270 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

Saturday, 28 May 2016 15:48

የነፃ ፕሬስ ጥግ

ሚዲያውን የሚቆጣጠር ሁሉ፣
አዕምሮንም ይቆጣጠራል፡፡
ጂም ሞሪሰን
- ሚዲያ እንደ ሌሎች ነገሮች ሁሉ
ሊገዛ ይችላል፡፡ ሁሉም ነገር የራሱ ዋጋ ያለው
ይመስላል፡፡ ነፃ ፕሬስም ጭምር፡፡
ላንስ ሞርካን
- ነፃ ፕሬስ ጥሩ ወይም መጥፎ ሊሆን
ይችላል፡፡ ነፃነት በሌለበት ግን ያለጥርጥር
መጥፎ ከመሆን ውጭ ሌላ ዕድል የለውም፡፡
አልበርት ካሙ
- በአገርህ ውስጥ ነፃ ፕሬስ ከሌለ
በቀር ጋዜጦችን መግዛትና ዜና መከታተል
አያስፈልግም፤ ምክንያቱም ውሸቶችን
ማዳመጥ አስፈላጊ አይደለም! አንድ ተጨባጭ
መረጃ እንደሆነ ታገኛለህ፡- በሚመሩህ ሰዎች
እየተታለልክ ነው! ይሄ ለአንተ በቂ መረጃ
ነው፡፡
ሜህሜት ሙራት አይልዳን
- ሁሉም ፀሐፊ የየራሱን ውሸቶች
ይናገር፡፡ ያ ነው የፕሬስ ነፃነት፡፡
ኖርማን ሜይለር
- በእኔ አስተያየት፣ የዲሞክራሲ
የማዕዘን ድንጋይ ነፃ ፕሬስ ነው፡፡
ሚሎስ ፎርማን
- ወደ ጋዜጠኝነት ሙያ የመጣነው
ታዋቂ ለመሆን አይደለም፡፡ እውነቱን
መፈለግን መልሶቹን እስክናገኝ ድረስ
በመሪዎቻችን ላይ የማያቋርጥ ጫና ማድረግ
ሥራችን ነው፡፡
ሔለን ቶማስ
- ጥሩ ጋዜጠኝነት፣ ጥሩ ቴሌቪዥን
ዓለማችንን የተሻለች የመኖሪያ ሥፍራ
ያደርጓታል ብዬ አምናለሁ፡፡
ክርስቲያኔ አማንፖር
- በጋዜጠኝነት የምታምን ከሆነ፣ ጥሩ
ጋዜጠኞችን አትሳደብም፡፡
ሲድኒ ስቻንበርግ
- ዓላማህ ዓለምን መለወጥ ከሆነ
ጋዜጠኝነት በጣም ፈጣኑ የአጭር ጊዜ መሳሪያ
ነው ብዬ አሁንም ድረስ አምናለሁ፡፡
ቶም ስቶፓርድ

ከ 300 ሺ በ ላይ ሶማሊያውያን ስ ደተኞችን ወደ አገራቸው ለመመለስ ወ ስናለች
          ኬንያ በአለማችን በትልቅነቱ ቀዳሚውን ስፍራ የሚይዘውን የዳዳብ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ ለመዝጋት መወሰኗን የአገሪቱ ምክትል ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ መግለጻቸውን ተከትሎ፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ውሳኔውን እንደሚቃወመው ማስታወቁን ኦል አፍሪካን ዶት ኮም ዘገበ፡፡
የተመድ ዋና ጸሃፊ ባንኪ ሙን፤ ኬንያ ግዙፉን የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ ለመዝጋት መወሰኗ፣ በመጠለያ ጣቢያው ውስጥ የሚገኙ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ስደተኞችን ለከፋ አደጋና ጥፋት የሚዳርግ በመሆኑ ውሳኔውን እንደሚቃወሙት ማስታወቃቸውን ዘገባው ጠቁሟል፡፡ የኬንያ ምክትል ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ ባለፈው ሰኞ በቱርክ መዲና ኢስታምቡል በተካሄደው የዓለማችን የሰብዓዊ ጉዳዮች ጉባኤ ላይ የአገሪቱ መንግስት የስደተኞች መጠለያ ጣቢያውን በመዝጋት 300 ሺህ ያህል ሶማሊያውያን ስደተኞችን ወደመጡበት ለመመለስ ያሳለፈው ውሳኔ የማይቀለበስ ነው ሲሉ መናገራቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ አለማቀፉ ማህበረሰብ ስደተኞቹን መልሶ ለማስፈር ተገቢውን ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪ ማቅረባቸውንም አመልክቷል፡፡ የኬንያ መንግስት የስደተኞች መጠለያ ጣቢያዎችን በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ለመዝጋት የወሰነው፣ የሽብርተኞች መደበቂያና ለአገሪቱ ደህንነት ስጋት በመሆናቸውና ለአካባቢው አደጋ ስለሆኑ ነው ማለቱን የጠቆመው ዘገባው፣ተመድ ውሳኔውን ተቃውሞታል፡፡

     በግል ህይወትም ይሁን በድርጅታዊ አሰራርና ዕድገት ውስጥ መሆን ያለበትና እየሆነ ያለው ለየቅል ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ ክስተት ደግሞ ብዙ ግዜ የሚያጋጥም ጉዳይ ነው፡፡ በርካታ ባለድርሻ አካላት ባሉባቸው ሰፊ ሃገራዊ ጉዳዮች ላይ ክፍተቱ ገዝፎ እንመለከታለን፡፡ እንደ ግለሰብ አንድ ሰው፣በህይወቱ ውስጥ መሆን ባለበትና እየሆነ ባለው ኩነት መካከል ሰፊ ልዩነት ሲኖረው፣ ወደ መፍትሔ የሚወስደው ተጨባጭ ርምጃ፣መጀመሪያ አሁን ያለበትን ሁኔታ በደንብ መረዳት፣ ቀጥሎም ምን መሆን እንዳለበት በግልፅ በማስቀመጥ ወደዛ የሚያደርሱትን መንገዶችና ስራዎች ብሎም በአጠገቡ ያሉ ሊያግዙት የሚችሉ አካላትን መለየት ይሆናል፡፡ አብዛኛው ሰው በየትኛውም አለም ይኑር ተመሳሳይ ሂደት ሲከተልም እናያለን፡፡ ይህ የለውጥ ሂደት ከግለሰብ ጀምሮ ለድርጅት፣ ለአገር ብሎም ለአለም የሚሰራ ነው፡፡ ለውጥ ለማምጣት ሙሉ ሂደቱን መጓዝ አለብን ፤ ግማሽ መንገድ ተጉዞ ሙሉ ውጤት ማምጣት አይቻልምና፡፡ ችግሩ በበርካታ ሃገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ የሚደረጉ ውይይቶች በአብዛኛዉ ባሉ ሁኔታዎች ላይ ብቻ በማተኮር መሆን ያለበትን ማስቀመጥ አለመቻላቸዉ ነዉ፡፡ ስለሆነም ቀጣዩና የሚፈለገዉ ሂደት መምጣት አለበት ፤ ውይይቶች ወደ ላቀ ደረጃ መሸጋገር አለባቸው፡፡ለምሳሌ ባለን የመገናኛ ብዙሀን ደስተኛ ካልሆንን ምን አይነት የመገናኛ ብዙሀን እንፈልጋለን? ያን የምንጓጓለትን የመገናኛ ብዙሃን ዕዉን ለማድረግስ ምን መስራት ይጠበቅብናል ብለን መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ በተመሳሳይ በአገራችን ያለው የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ዘርፍም የዚህ የውይይቶች ግማሽ መንገድ ላይ መቆም ችግር ማሳያ ነው፡፡ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት፣ ደጋፊ አካላት፣ የመገናኛ ብዙሀን፣ ምሁራን፣ የንግዱ ማህበረሰብ
ብሎም መላው ህብረተሰብ፣ በአገራችን ባለው የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ዘርፍ (ሲቪክ
ማህበራት) ደስተኛ እንዳልሆኑ ይገልፃሉ፡፡ የበጎ አድራጎት ድርጅት አሰራር ከፅንሰ ሀሳቡ አንፃር መሆን ያለበትና እየሆነ ያለው ይለያያል የሚል አስተያየት ከብዙ አቅጣጫ ይደመጣል፡፡ በበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት በኩል ደግሞ መንግስትና የመገናኛ ብዙሀን ለስራችን ተገቢውን እውቅና አይሰጡም በማለት ይወቅሳሉ፡፡ እነዚህ አስተያየቶች ከፊል እውነታ ሊኖራቸው ይችላል፡፡ ዋናው እውነታ ግን ውይይቱ ግማሽ ሂደት ላይ መቆሙ ነው፡፡ ይህ ማለት ከላይ የተዘረዘሩት ሁሉም አካላት በአገራችን ባለው የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ደስተኛ ካልሆኑ ቀጥሎ መምጣት ያለበት እና መሆን ያለበት ምንድነው? ምን አይነት የበጎ አድራጎት ድርጀቶችና ማህበራት ዘርፍ መፍጠር እንፈልጋለን? ምን መደረግስ አለበት? ከማን ምን ይጠበቃል? ወደሚል ሰፊ የውይይትና የመፍትሔ ደረጃ ማደግ ይኖርበታል፡፡ የአመለካከት ችግሩ የሚጀምረው የዘርፉን ሚና አሳንሶ ከማየት ነው፡፡ ይህ ክፍተት ሚናቸውን ከሚያመጡት ገንዘብ መጠን ጋር በዋናነት በሚያያይዙት የበጎ አድርጎት ድርጅቶችና ማህበራት ይጀምራል፡፡ መንግስት በበኩሉ ደግሞ ከዕለት ምጽዋት ጋር በሚመሳሰል መልኩ በጎ የማድረግ ስራ ብቻ አላቸው ብሎ ያስባል፡፡ ይህ የመንግስት አመለካከትም የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት
ወሳኝ የልማት አጋር ናቸዉ ከሚለዉ ብሂል ጋር ይጋጫል፡፡ ይህ ፅሁፍም እየሆነ ባለው ላይ ያተኮረ
ስላልሆነ ወደ ቀጣይና  የተሻለ ደረጃ እንዴት እንሸጋገር የሚለዉ ላይ ገንቢ ትንተና ያደርጋል፡፡
በእርግጥ ይህ ፅሁፍ ምን መሆን እንዳለበት በቀጥታ የማስቀመጥ አላማም ሆነ አቅም የለውም፡፡
የዚህ ፅሁፍ አላማ ውይይቶችን ማሻሻል ነው፤እየሆነ ባለው ላይ ከመወቃቀሰ ይልቅ መሆን
ወዳለበት እንድንመለከት ጥያቄውን ማንሳት ነው፡፡
መንግስት ምን አይነት የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ዘርፍ ነው መፍጠር የሚፈልገዉ?
ሁላችንንም የሚያስደስተንና እንደ አገር የምንኮራበት ዘርፍ ለመፍጠር መንግስት ምን ለማድረግ
አቅዷል? እንደመፍትሄ ሃሳብም ዘርፍ መሻሻልና ማደግ ካለበት መሪ ይፈልጋል፤ስለዚህ መንግስት
ሴክተሩን የመምራትና የማገዝ ሃገራዊ ግዴታ አለበት፡፡ ይህ ማለት የዘርፉ ነፃነት እንደተጠበቀ ሆኖ፣
መንግስት የመንግስት ሚናውን በመወጣት ለዘርፉ የተሻለ የስራ ማዕቀፍ በመፍጠር ረገድ ከፍተኛ
ድጋፍ ማድረግ አለበት ማለት ነው፡፡
የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ሀላፊዎች በበኩላቸዉ፤በጎ የማድረግ ፅንሰ ሀሳብንና አሁን
በተግባር እየሆነ ያለውን ማነጻጸርና ራስን መገምገም፣ ከዚህ አልፎም መሆን ወዳለበት አቅጣጫ
መምጣት ይኖርባቸዋል፡፡ ማህበረሰባችን አሉታዊም ሆነ አዎንታዊ ዕይታዎችን
የሚያንጻባርቀዉ፣ከሚያየዉና ከሚሰማዉ በመነሳት ነዉ፡፡ ስለሆነም አሉታዊ አመለካከት ቢኖር
ሁልጊዜ ስህተት ነዉ ለማለት ያስቸግራል፡፡ የበጎ አድራጎት ድርጅት ውስጥ መስራት ማለት ጥሩ
ደሞዝ ከማግኘት የዘለለ ትርጉም እንዳለው በአሰራራቸንና አኗኗራችን ማሳየት አለብን፡፡ ዋናው
ጉዳይ የሚኮረኩረን ፣የማያስተኛንና የተነሳንበት ዓላማ ህዝብን የመደገፍና የመርዳት ብሎም
የመንግስትና የህዝብ ወሳኝ የልማት አጋር መሆናችንን ማስረገጥ ላይ ነዉ፡፡ የበጎ አድራጎት ድርጅት ሀላፊ፤በህብረተሰቡ በበጎ ስራው እና ተግባሩ የሚከበር መሆን ያለበት ሲሆን አሁን ያለው አመለካከት ግን ሙሉ በሙሉ ከዚህ ጋር አብሮ ይሄዳል ለማለት ያስቸግራል፡፡ ይህ ማለት ግን ማህበረሰባችን በሙሉ ተመሳሳይና ለሴክተሩ የተዛባ አመለካከት አለዉ ማለት አይደለም፡፡ መልካም የሚሰሩ እጅግ በርካታ ቁጥር ያላቸዉ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት እንዳሉ ሁሉ፣ በአግባቡ የማይሰሩ የሴክተሩን ስም ጥላሸት የሚቀቡ በጣም ጥቂት ድርጅቶች እንዳሉም ይታመናል፡፡ይህን ጉዳይ ከስር መሰረቱ ስንመረምረው፣ማየት ያለብን በአገራችን መፍጠር የምንፈልገውን ዘርፍ አሁን ካለበት ደረጃ ጋር በማነፃፀርና የህዝባችንን አኗኗር፣ ባህልና ወግ ግምት ዉስጥ በማስገባት እንጂ በቀጥታ ከሌላ አገር ጋር በማነፃፀር መሆን የለበትም የሚል ዕምነት አለን፡፡ ይህ ማለት ግን ጠቃሚ ተሞክሮዎች ከዉጭ አይወሰዱም ማለት አይደለም፡፡ በማንኛዉም ሰአትና
ጊዜ አገራችንን እና ህዝባችንን የበለጠ ተጠቃሚ ሊያደርግ የሚችል የአሰራር ስርአት ቢኖር ልምድ
መወሰዱ በበጎ ጎን የሚታይ ነዉ፡፡  የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ከተለመደው የበጎ አድራጎት ስራ በዘለለ በአገራችን ሁለንተናዊ ዕድገት ውስጥ ብዙ ሚና መጫወት ይችላሉ፤አለባቸውም፡፡ የሙያ ማህበራት የአንድን ሙያ ጥራት ከመጠበቅ እና ከማሳደግ አንፃር ትልቅ ስራ መስራት ይችላሉ፡፡ የተለያዩ አገር አቀፍ ህጎችና ፖሊሲዎች ሲወጡ ከሙያቸው ጋር በተያያዙ ጉዳዮች ዙርያ ጠቀሚ ግብአቶች መስጠት ይችላሉ፡፡ የተለያዩ ሀገራዊ እና ህዝባዊ የለውጥ ንቅናቄዎች ለማምጣት ሰንፈልግ የብዙሀን ማህበራት ንቅናቄውን መምራትና ማቀጣጠል ይችላሉ፤ ሌላም ሌላም፡፡  መንግስት አንድን አገር ሲመራ ሁሉንም ዘርፍ በእኩል መምራት ይጠበቅበታል፡፡ ይሄም በወሳኝ መልኩ ተቀራርቦ መስራትን ይጠይቃል፡፡ በዋናነት የአሰራር አቅጣጫ ከሚያስቀምጠው ከፍተኛው አመራር ማለትም፤ ከጠቅላይ ሚኒስትራችን ምን አይነት የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት መፍጠር እንደሚፈልጉና ምን ምን እንዳቀዱ ማወቅ እንሻለን፤ይህ የሚሆንበት አሰራር መፈጠር አለበት፡፡ ከሙያ ማህበራት ጋር በተያያዘ የተለያዩ የሙያ ማህበራት እንዳሉ በራሱ ግንዛቤ የለም፡፡ ለምሳሌ
የጋዜጠኞች ማህበር፣ የሙዚቀኞች ማህበር፣ የሰአሊያንና ቀራፅያን ፣ የፊልም ሰሪዎች፣ የደራስያን
ወዘተ እያለ ይቀጥላል፡፡ ዘርፉ ይህን ሁሉ ይዞ ነው ሚናውን አሳንሰን እያየን ያለነው፡፡ ለእነኚህ
አካለትም የተመቻቸ የአሰራር ስርአት መፍጠር፤ ስራዎቻቸዉን ማየትና መገምገም፣ ለአሰራር
የማያመቹ ሁኔታዎችን በጋራ መለየትና መፍትሄ ማበጀት ሌላዉ የመንግስት ወሳኝ የስራ ሃላፊነት
ነዉ ተብሎ ይታመናል፡፡ ከዚህ ባለፈ በአገራችን የሚገኙ ደጋፊ አካላትም አሁን ባለው ዘርፍ ብዙም ደስተኛ አለመሆናቸውን ሲገልፁ ይደመጣል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት በኩል የደጋፊ አካላት የአሰራር ስርአቶች በተለይም ለሃገር በቀል ድርጅቶች የማያመቹና ይልቁንም ዉስብስብ መሆናቸዉ ይገለጻል፡፡ ይህም “እንዳያማህ ጥራዉ፣እንዳይበላ ግፋዉ” የሚለዉን የአባቶች ብሂል ያስታዉሰናል፡፡ ስለሆነም
ደጋፊ አካላት የሚያደርጉት እገዛ፣ የተሻለ ለውጥ ማምጣት እንዲችል ከታመነ በተለይም አገር በቀል
ድርጅቶች ያላቸዉን ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ ግምት ዉስጥ በማስገባት ለህዝብ እጅግ የቀረቡ
በመሆናቸዉ ይህንኑ መጠቀም መቻል ብልህነት ነዉ፡፡ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት:
መንግስትና የንግዱ ማህበረሰብ በጋራ የምንጋራው ዓላማና ራዕይ ይዘን ነገር ግን የተለያየ ሀላፊነት
ያለብን ባለ ድርሻ አካላት እንጂ ለብቻችን ተነጥለን የምንሰራው ስራ እንደሌለ በመገንዘብ፣ ተቀራርቦ ወደ መስራት በመምጣት ጠንካራ ዘርፍ መፍጠር እንደምንችል እናምናለን፡፡ የበጎ አድራጊነት ፅንሰ ሀሳብና አሁን የምንንቀሳቀስበትን ማዕቀፍ በመፈተሸ፣ ከፅንስ ሀሳቡ ጋር የሚሄድ አሰራርና እንቅስቃሴ መፍጠር መቻል አለብን፡፡ እነዚህንና በተጨማሪም እናንተ አንባብያን ባለድርሻ አካላት ምትጨምሩዋቸው ሀሳቦችን አንድላይ በማምጣት አሁን ካለን ደካማ የሆነ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ዘርፍ ወደምንፈልገው እና መሆን ወዳለበት መውሰድ እንደምንችል ጠንካራ እምነት አለን፡፡ ይሄም የሚጀምረው ጉዳዩን ወደ ጋራ ውይይት በማምጣት ሲሆን ፤ ሂደቱን  ሀ ብለን ይሄው ዛሬ በዚህ ፅሁፍ ጀምረነዋል፡፡











Saturday, 28 May 2016 15:27

ቬንዝዌላ - የቅዠት አገር

አገሪቱ ለሃብታሙም ለድሃውም ሲኦል ሆናለች፡፡ የፋብሪካ ባለቤት መሆን፣ እዳ ነው፡፡ ትንሽዬ ምግብ ቤት ከፍቶ መስራት እንኳ፤ ትዕግስትን ያስጨርሳል፡፡ በየአመቱ ሰላሳ አይነት የስራ ፈቃዶችን ለማሳደስ መንከራተት የግድ ነው፡፡
ለአንድ ምናብ ቤት ወይም ለአንድ ፋብሪካ ሰላሳ የፈቃድ እድሳት! እንኳን ሰላሳ፣ አንዱን የስራ ፈቃድ ብቻ ማሳደስም መከራ ነው፡፡ ቢቢሲ ያነጋገረው የፋብሪካ ባለቤት፣ በየእለቱ ከሚያጋጥሙት መዓት መከራዎች መካከል፣ ቀላል የሚመስል አንድ ችግር ብቻ በመጥቀስ አስረድቷል፡፡ የመንግስት የቁጥጥር ብዛት አይጣል ነው፡፡
ፋብሪካው በየወሩ ለሰራተኞች “ሶፍት” መስጠት አለበት በሚል የሚደረግ፣ ቁጥጥር ብቻ፣ መከራውን አይቷል፡፡ “ሶፍት” እንደማንኛውም ሸቀጥ፤ በመንግስት ሱቆች ነው የሚቀርበው፡፡ ባለፋብሪካው፣ ቀኑን ሙሉ ወረፋ ይዞ፣ ሁለት ሦስት ሶፍት መግዛት ይችላል - እድለኛ ከሆነ፡፡ ብዙ ጊዜ አይገባኝማ፡፡ ወዲያው ያልቃል፡፡ ሌላኛው አማራጭ፣ በኮንትሮባንድ የገባ ሶፍት መግዛት ነው፡፡ ነገር ግን የኮንትሮባንድ “ሶፍት” መግዛቱ ከታወቀ፤ ከመከራ አያመልጥም - ፋብሪካው ይወረስበታል፡፡ ለሰራተኞች ሶፍት ካላቀረበም፣ ፋብሪካው በመንግስት ይወረሳል፡፡
ማምለጫ የለውም፡፡ ሶፍት እስኪገኝ ድረስ የፋብሪካውን ስራ ለማስቆም ሲገደድ አስቡት፡፡
ግን ይህንንም ማድረግ አይችልም፡፡ ስራ ያቆመ ፋብሪካ በመንግስት ይወረሳል የሚል ህግ ታውጇል፡፡
ቢቢሲ እንደዘገባው፣ የቬንዝዌላ መንግስት ሶሻሊዝምን አስፋፋለሁ በማለት፣ ከአንድ ሺ በላይ ፋብሪካዎችን ወርሷል፡፡ ፋብሪካዎቹን ምርታማ አደርጋለሁ ብሎ ነው የወረሳቸው፡፡ ግን አልቻለም፡፡ አብዛኞቹ የመንግስት ፋብሪካዎች እየሰሩ አይደለም ብሏል - የቢቢሲው ጋዜጠኛ፡፡
የምርትና የሸቀጦች እጥረት እንዲህ እየተባባሰ፣ አገሪቱ ዛሬ ገደል አፋፍ ላይ ደርሳለች፡፡
ነዋሪዎችን በማነጋገር ከቬንዝዌላ ዘገባ ያቀረበችው የሲኤንኤን ጋዜጠኛ፣ የሚላስ የሚቀመስ ምግብ እየጠፋ ነው ብላለች፡፡ በዋጋ ቁጥጥር ሳቢያ፣ ሸቀጦች ሁሉ ከገበያ ጠፍተዋል፡፡
እናም የአገሬው ሰዎች፣ ዘይትና ዱቄት፣ ጨውና ስኳር፣ ቲማቲምና ሳሙና ለመግዛት ከመንግስት ሱቆች ደጃፍ ከንጋት እስከ ምሽት ይሰለፋሉ፡፡ የሱቁ ደጃፍ ላይ የተጀመረው ወረፋ፣ ጥጋጥጉን እስከ ማዶ ሄዶ፣ መስቀለኛው መንገድ ላይ ወደ ግራ ታጥፎ፣ ሩቅ ጫፍ ድረስ ይቀጥላል፡፡
ከአምስት ሰዓት በኋላ ወረፋ የደረሰው ጐልማሳ፣ ዱቄትና ወተት አላገኘም፡፡ ቢጨንቀው፣ ሁለት ሊትር ክሬም ገዝቶ ወጣ፡፡
 ሌላ ነገር የለም፡፡ ከሦስት ቀን በኋላ ተመልሶ እድሉን ይሞክራል፡፡ በየቀኑ መሄድ አይቻልም፡፡ በሳምንት ሁለት ቀን ብቻ ነው የሚቻለው፡፡ የአንዱ ቤተሰብ ተራ፣ ሰኞና ሃሙስ ሊሆን ይችላል፡፡
የሌላኛው ቤተሰብ ደግሞ ማክሰኞና አርብ፡፡ አንዳንድ የባሰበት እድለ ቢስ፣ ዛሬ የወዛደሮች በዓል ዋዜማ ነው ተብሎ ቀኑ ያልፍበታል፡፡ሆስፒታሎችና ፋርማሲዎችም እንዲሁ፣ የመድሃኒት መደርደሪያቸው ኦና ሆኗል፡፡ ስካይ ኒውስ ረቡዕ እለት ባቀረበው ልዩ ዘገባ፣ የዋና ከተማዋን ሆስፒታሎች አሳይቷል፡፡
የምርመራ መሳሪያዎች አይሰሩም - በየኮሪደሩ ተወዝፈዋል፡፡ የምርመራና የታማሚዎች ክፍሎች፣ ኮሪደሮችና መፀዳጃ ቤቶች ቆሽሸው ይዘገንናሉ፡፡ ውሃ የለም፡፡
የህመም ማስታገሻና አሞክሳስሊን የመሳሰሉ ተራ መድሃኒቶች እንኳ ብርቅ ሆነዋል (ከውጭ አገር ፓናዶልና አሞክሳስሊን ገዝቶ የሚልክ ወዳጅ ዘመድ ካልተገኘ በቀር) የ21ኛው ክፍለ ዘመን የሶሻሊዝም አብዮተኛ ነኝ የሚል መንግስት፣ ቬንዝዌላን የቅዠት አገር አድርጓታል፡፡
 አሳዛኙ ነገር፣ እንዲህ አይነት መንግስት በምርጫ አሸንፎ ስልጣን መያዙ ነው፡፡