
Administrator
ለመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች በሙሉ እንኳን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ
በትንባሆ የተገዛ ጦር እገበያ መሀል ቢወረውሩት ጓያ ጫፍ ላይ ይቆማል!
ዕንቁራሪቶች፣ ጦጣዎች፣ አይጦችና የዱር አራዊቱ ንጉስ አንበሳ የሚኖሩበት ትልቅ ደን አለ፡፡ እንቁራሪቶቹ ከደኑ አጠገብ ካለው ኩሬ ውስጥ ነው የሚኖሩት፡፡ አንበሳ የሚጠይቃቸውን ሁሉንም በመታዘዝ ነው ሌሎቹ የሚኖሩት፡፡ አንድ ቀን እንቁራሪቶቹ፣ ጦጣዎቹና አይጦቹ አንድ ላይ መስክ ላይ በየበኩላቸው እየለቃቀሙ ሳለ፣ አዳኞች አንበሳውን ሲያሳድዱት ተመለከቱ፡፡ እንቁራሪቶቹ “ለጌታም ጌታ አለው! ሰው’ኮ የአንበሳ ጠላት ነው አይለቀውም፡፡ ከዚህ መዓት ለማምለጥ በሉ ወደ ኩሬያችን እንሂድ” አሉና ወደ ኩሬያቸው አመሩ፡፡ አይጦቹም፣ የደኑ ገዢ አንበሳ ነው ብለው ስለያሚስቡ፣ “ሰዎችና አንበሶች አጥፊና ጠፊ ናቸው፡፡ የዚህ አንበሳ ጣጣ ለእኛ እንዳይተርፈን በጊዜ ወደ ጎሬያችን ገብተን እንሸሸግ” አሉና ሄዱ፡፡ ጦጣዎቹ “ሰው አንበሳ ሲጠላ እንድ ጉድ ነው፡፡ በጊዜ ዛፋችን ላይ እንውጣ” ብለው በየዛፎቻቸው ላይ ተንጠላጥለው ወጡ፡፡
አዳኞቹ አንበሳውን ገድለው ቆዳውን ገፍፈው ወሰዱ፡፡ አዳኞቹ ከሄዱ በኋላ ዕንቁራሪቶቹ ጦጣዎቹና አይጦቹ እንደገና ተሰባስበው፤ ጦጣ ስለ ዛፍ ላይ ኑሮ፤ እንቁራሪት ስለ ኩሬ ኑሮ፣ አይጥ ስለ ከመሬት በታች ኑሮ አወጉና የአንበሳውን አሟሟት እያነሱ በየበኩላቸው የሚያስተዳድሩት ግዛት እንዳላቸው በመጥቀስ ወጋቸውን ሲሰልቁ ቆዩ፡፡
በነጋታው በኩሬ ውስጥ ያሉትን ነብሳት ሁሉ ለመብላት የሚፈልጉ አጥማጆች ሲመጡ ጦጣዎች ወደ ዛፋቸው፣ አይጦት ወደ ጉድጓዳቸው ሮጡ፡፡ እንቁራሪቶች ግን ሁሉም ከኩሬው ተለቃቅመው ተወሰዱ፡፡ ጦጣዎችና አይጦች እንደ ልማዳቸው በሦስተኛው ቀን ተገናኝተው እያወጉ “እንቁራሪቶቹን ምን አድርገዋቸው ይሆን?” እያሉ ተጠያየቁ፡፡ “ሰው እኮ ጨካኝ ነው፡፡ በልቶዋቸው ይሆናል” አሉ ጦጣዎቹ፡፡ “ምናልባት እሰኪበላቸው በእንክብካቤ ያኖራቸው ይሆናል” አሉ አይጦቹ፡፡
ይህንኑ እያወጉ፤ ሳሉ የአይጥ ወጥመድ የያዙ በርካታ ሰዎች መምጣታቸውን አዩ፡፡ ጦጣዎቹ ፈጥነው ወደዛፋቸው ወጡ፡፡ አይጦቹ ወደ ጉድጓዳቸው ሮጡ፡፡ ባለወጥመዶቹ አድፍጠው ወጥመዶቸውን በጥንቃቄ በየጉድጓዳቸው አፋፍና ውስጥ አኖሩባቸው፡፡
በነጋታው አይጦች የወጥመዶቹ ሲሳይ ሆኑ፡፡
ጦጣዎችን “አንበሳው ሰው ጠላቱ መሆኑን ረስቶ ጉልበቱን ተማምኖ በደን ውስጥ ሲጎማለል ተበላ፡፡ ዕንቁራሪቶቹም ማምለጫ በሌለው ኩሬ ውስጥ እንደተወሸቁ መውጫ ሳያበጁ ቀለጡ፡፡ እነዚህ አይጦችም ገብተው ከማይወጡበት ጉድጓድ ውስጥ ተቀርቅረው ብቅ ሲሉ በወጥመድ እየታነቁ ሲጥ አሉ፡፡ እኛ ግን ዛፍ ላይ ነንና ሰው ወደኛ ሲመጣ ወደታች በቀላሉ ስለሚታየን ከዛፍ እዛፍ እየዘለልን ደብዛችንን እናጠፋበታለን” ተባባሉ፡፡
ጥቂት ቀናት ሰነባብቶ ሰዎች ወደጫካው መጡ፡፡ ጦጣዎቹ ማንም አይነካን ብለው ዛፋቸው ላይ እንዳሉ ቆዩ፡፡
የሰው ልጅ ጥፋት ሰለባ መሆናቸውን ያወቁት ግን ከዳር ዳር ደኑ በእሳት መያያዙን ያዩ ጊዜ ነበር፡፡ ዛፍ ላይ ያሉት እዚያው እንደተንጠለጠሉ ተቃጠሉ፤ የወረዱትም በሰው እጅ አለቁ፡፡ የሚገርመው ግን አዳኞቹ ሰዎች ወደ ቤታቸው ሲመለሱ በጠላቶቻቸው ተቃጥሎ ዶግ-አመድ ሆኖ አገኙት፡፡
* * *
ዓለም የአጥፊና ጠፊ መድረክ ናት፡፡ ነግ በኔ ብሎ ገና በጠዋት ያልተጠናቀቀ ዕጣ-ፈንታው እንደቀዳሚዎቹ ሟቾች ነው፡፡ የፋሲካው በግ፣ በገናው በግ እንደሳቀ መሞቱ ከዓመት ዓመት የምናየው ሀቅ ነው፡፡ እኔ የራሴን ታሪክ እሰራለሁኝ እንጂ ሌሎች እኔን መሰሎች በታሪክ ውስጥ ምን ጽዋ ደረሳቸው? ብሎ አለመጠየቅ፣ ምላሹን ካገኙም የእኔንስ ክፉ-ዕጣ እንዴት እመክተዋለሁ? ብሎ አለማውጠንጠን የዓለምንም የሀገራችንንም የፖለቲካ ድርጅቶች ቡድኖች፣ መሪዎችና ታዋቂ ግለሰቦች ታሪካዊ ዕጣ-ፈንታ ሳይታለም የተፈታ እንዲሆን ካደረገው ውሉ አድሯል፡፡ ነግ-በኔ አለማለት ክፉ እርግማን ነው፡፡
ለማርቲን ኒየሞይለር መታሰቢያ የተደረገው ጽሁፍ ይሄንኑ ይነግረናል፡፡ ማርቲን ኒየሞይለር (1892-1984) የፕሮቴስታንት ክርስቲያን የነበረ ጀርመናዊ ቄስ ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ውስጥ ናዚዎችን በመቃወም ከባድ ዘመቻ በማካሄዱ እ.ኤ.አ ከ1938 እስከ 1945 ዓ.ም ለ8 ዓመታት ማጎሪያ ካምፕ ውስጥ አስገብተው ሲያሰቃዩት ከርሞ ኋላ ተፈትቶ ከ1961 እስከ 1968 ዓ.ም ለሰባት ዓመታት የአለም አብያተ-ክርስቲያናት መማክርት ፕሬዚዳንት ሆኖ የመራ ጠንካራ ሰው ነበር፡፡ ለሱ መታሰቢያ የተደረገው ፅሁፍ እነሆ፡-
በጀርመን ናዚዎች መጥተው በመጀመሪያ ያጠቁት ኮሙኒስቶቹን ነበር፡፡ የኮሙኒስቶቹን በር እያንኳኩ ለጨፈጭፏቸው እያየሁ እኔ ዝም አልኩ፡፡ ምክንያቱም ኮሙኒስት አልነበርኩም፡፡
ቀጥለው አይሁዶቹን ወረዱባቸው፡፡ የአይሁዶቹን በር ሲያንኳኩም እኔ ዝም አልኩ፡፡ ምክንያቱም እኔ አይሁድ አይደለሁም፡፡
ከዚያ ወደ ሰራተኛ ማህበራቱ ዞሩ፡፡ የሰራተኞቹን በር ሲያንኳኩም እኔ ጭጭ አልኩ፡፡ ምክንያቱም የሰራተኛ ማህበሩ አባል ስላልነበርኩ አይመለከተኝም፡፡
ቀጥለው ካቶሊኮቹ ይፈጁ ጀመር፡፡ የካቶሊኮቹንም በር ሲያንኳኩ አሁንም እኔ ዝም አልኩ፡፡ ምክንያቱም እኔ ፕሮቴስታንት ስለሆንኩ አይመለከተኝም፡፡
በመጨረሻ የእኔን በር አንኳኩ፡፡ በዚያን ሰዓት ግን ተነስቶ ሊናገር የሚችል ምንም ሰው አልተረፈም ነበር፡፡
(ለማርቲን ኒየሞይለር [ፍሬድሪሽ ጁስታቭ ኤሚል]መታሰቢያ የተፃፈ- 1949)
የፈለገው መንግስት ይመቸኛል ባለው መንገድ ያሻውን ሀገር ሲረግጥ ያሻውን መሳሪያ ሲጠቀም፣ በእኔስ ላይ ፊቱን ያዞረ እለት ምን ይውጠኛል? የእኔስ በር የተንኳኳ እለት ማን አብሮኝ ይቆማል? ብሎ አለመጠየቅ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ ዛሬ በየቻናሉ በቀጥታ ሥርጭት በቴሌቪዥን የምናየው ጦርነት እንደተዋጣለት የሲኒማ አሊያም የቴያትር ዝግጅት የውሸት እልቂት እስኪመስል ድረስ ያስገርማል፡፡ በዓለም ታሪክ የመጀመሪያው ሳይሆንም አይቀር፡፡ የጋዜጠኞቹም ድምጽት “ጦርነቱ ሊጀመር ነው አብረን እንከታተል” እንደማለት ሆኗል- የሰው ልጅ ሞት ምፀት! እንደትላንት ወዲያ “ኢምፔሪያዝም ውርደት ቀለቡ ነው”… የሚባልበት የቀዝቃዛው ጦርነት ዘመን አልፎ፤ እፎይ ብሎ አለም ለመተንፈስ አለመቻሉ ከመደገም የማይቀሩ ብዙ የታሪክ ስላች መኖራቸውን ያስገነዝበናል፡፡ እግረ-መንገዱንም ሀያላን መቼም በቃኝ እንደማያውቁ ዳግም ያስታውሰናል፡፡ የወታደራዊ ኃይል ግሎባላይዜሽን የት እንደሚደርስም ይጠቁመን ይሆናል፡፡ “ወተት ሰርቆ ከመጠጣቱ ይልቅ አፍ አለመጥረጉ ያሳፍረዋል” እንዲሉ ትላልቁን የሃያላን ጥፋት ትቶ በእንጭፍጫፊ ላይ ማተኮር ሌላ ጥፋት እንደመፈፀም መሆኑን ሳያስገነዝበን አያልፍም፡፡ ትንሹን አምባገነን ትልቁ አምባገነን፣ ሚጢጢውን ጉልበተኛ ግዙፉ ጉልበተኛ ሊውጠው ይመኛል፡፡ ይንጠራራል፡፡ ይስፋፋል፡፡
እስከዚያ እንቅልፍ የለውም፡፡ ህዝቡና አገሩ ከመጤፍ አለመቆጠሩ ግን የየዘመኑ ትራጀዲ ነው፡፡ የዛሬም፡፡ ታዋቂው ገጣሚ መንግስቱ ለማ “ባንተ አልተጀመረም ያዳሜ ምኞት” “ከተጠቃውሚ ’መራቅ‘ አጥቂን ‘መጠጋት’ የሚለውን እንደመርህ የያዘው በርካታ መሆኑ ደግሞ መራር ትራጀዲ ያደርገዋል፡፡ “ጠባይ ያለው ልጅ ኑክሊየር ይሰጠዋል፡፡ ጠባይ የሌለው ልጅ የአሻንጉሊት ሽጉጡንም ይነጠቃል ዓይነት ሆኗል የሃያላኑ የአባትነት ባህሪ፡፡ [ወይም በግልባጩ ጠባይ ያለው ብልጥ ልጅ አየሩን ለበረራ ይፈቅዳል፡፡
ጠባይ የሌለው ልጅ “በሳዳም የመጣ በእኔ መጣ” ይላል፡፡ ሁሉንም ጠባይ ይዞ የተፈጠረው ደግሞ “ሳዳምንና አሜሪካን ያየ በኑክሊየር አይጫወትም” እያለ ከዛም ነዳጅ እየገዛ፣ ለዚህም ማዕድኑን እየቸረ ይቀመጣል፡፡ ማለትም ያስኬዳል] ጉዳዩ ግን የእኔን በር እስለካላንኳኳ ድረስ “ለእኔን አገር አማን ነው” ብሎ ማሰብ መተው ይጠይቃል፡፡ ሃያላን አልጠግብ ማለታቸው የስር መሰረት ነውና፡፡
የሐያላኑን ተወት አርገን አገራችን ስንገነባም፣ ነግ-በኔ ቁልፍ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ሌላ አገር ሲጠቃ ምን ግዴ ማለት ሌላ ፓርቲ ሲገፋ ምን ቁቤ ማለት፣ ሌላ ሰው ሜዳ ሲወድቅ እንደፍጥርጥሩ ማለት ቀን የጨለመ እለት ክፉ ነገር ነው፡፡ ትላንት በራሳችን መጥነንና ለክተን ያሰፋነውን የድንጋጌና የመርህ መጎናፀፊያ ዛሬ ዳር እስከዳር አገሬውን ካላለበስነው ብለን የምንታገልበት ሁኔታ የኋሊት ጉዞ ይመስላል፡፡ “ትንሽ ስንቅ የያዘ አስቀድሞ ይፈታል” እንዲሉ፡፡ አገርን የሚያህል ሰፊ ባህር፣ የትንጧን ህልማችንን መፍቻ ለማድረግና አንዲቷን ቀጭን ኩታችንን ለልጁም ላዋቂውም አለብሰዋሁ ብሎ አይሆንም ሲባሉ ግትር ማለት ደግ አይደለም፡፡ ቢያንስ የዋህነት ሲበዛ በሰፊው ተወጥሮ መሰነጣጠቅ ነው ውጤቱ፡፡ ሌላ አስቸጋሪ አባዜ የካፒታሊዝምን ሠሪ-አካል፣ በሶሻሊስት ልብ አንቀሳቅሰዋለሁ እንደ ማለት ያለ በውዥንብር የተሞላ መንገድ ላይ የምንራመድ ከሆነ “አንድ በአንድ ተንጠባጥበን እስክንጠፋ የዓላማ ጽናት እናሳያን” ወይም በወትሮው አባባል “እስከመጨረሻው አንድ ሰው እንታገላለን”… “የአብዮቱ ባቡር ፈጣን ው” እየተባባልን በሀገር እየተሳለቅን እንዳንከርም ነግ በኔን ማስተዋ ይበጃል፡፡
“ከቆየን አንድ ዓመት፣ ከበላን የተከለከለ ሣር!” እንዳለችው ላም በድርጅዊ አሰራርና ወገናዊነት በዘመዳምነት፤ በእከክልኝ-ልከክልህ፣ በአራዳነት፣ በወደቀው ዛፍ ምሳር በማብዛት፣ በዕቁብም በዕቁባትም በመመነዛዘር ለጌዜው ሙስናን ቢያስፋፉ የሥር የመሰረት ብቅ በሚልበት ሰዓት ምነው አፉን በቆረጠው ምነው እግሬን በሰበረው፣ ማለትን አሊያም የተሰራንበት ንጥረ ነገር በምንም ዓይነት ካባ ብንሸፍነው የማታ ማታ ብቅ ማለቱ ከቶ አይቀርም፡፡ “በትንባሆ የተገዛ ጦር፣ እገበያ መሀል ቢወረውሩት፤ ጓያ ጫፍ ላይ ይቆማል” የሚለው የወላይታ ተረትም የሚነግረን ይሄንኑ ነው፡፡
እንኳን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል አደረሳችሁ - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓልን አስመልክተው የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የገና በዓልን አስመልክቶ ያስተላለፉት መልዕክት ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ይቀርባል፡-
ቅዱሳት መጻሕፍት እንደሚነግሩን ሕግ ጥሶ ከእግዚአብሔር ጋር የታጣላው ራሱ የሰው ልጅ ነበረ፡፡ ዕርቅን አውርዶ ሰላምን ለማስፈን በረት ድረስ የመጣው ግን እግዚአብሔር ነው፡፡ እንደ ቅዱሳት መጻሕፍት አስተምህሮ እግዚአብሔር ሁሉን ቻይ፣ አሸናፊ፣ የሚሳነው አንዳች የሌለ ነው፡፡ ነገር ግን ለዕርቅ እና ለሰላም ሲል ወደ ማይገባው ሥፍራ መጣ፡፡ አሸናፊ ቢሆንም እንደ ተሸናፊ ሆነ፡፡ ዐቅም ቢኖረው እንደ ዐቅመ ቢስ ሆኖ ታየ፡፡ በሁሉ ሀብታም ሲሆን፣ ራሱን ታናሽ አደረገ፡፡ ይህ ሁሉ ለዕርቅና ለሰላም የተከፈለ የታላቅነት ዋጋ ነው፡፡
እግዚአብሔር ለዕርቅ እና ለሰላም ሲል በደካማዋ ከተማ በቤተልሔም፣ በተናቀችው ሥፍራ በበረት መገኘቱ የገባቸውም ያልገባቸውም ነበሩ፡፡ የገባቸው፤ ከሰማየ ሰማያት ወርደው “ሰላም እና ዕርቅ በምድር ይሁን” ብለው ዘመሩ፡፡ የገባቸው፤ ከምሥራቅ ኮከቡን አይተው፣ እጅ መንሻውን ይዘው መጡ፡፡ የገባቸው፤ በረታቸውን ለቅቀው ለድንግል ማርያም እና ለኢየሱስ ክርስቶስ ሰጡ፡፡ የገባቸው፤ የሰማይ መላእክቱን ተከትለው ወደ በረት ሄደው እርቅና ሰላምን አመሰገኑ፡፡
አቶ ቡልቻ ደመቅሳ በማረፋቸው የተሰማኝን ኀዘን እገልጻለሁ።
በሚችሉት ሁሉ ሀገራቸውንና አፍሪካን ያገለገሉ፣ በአቋማቸው ጽኑ፣ ሕዝቦችን ለማቀራረብ የተጉ፣ እውነት ነው ብለው ያመኑትን የትምና መቼም የሚናገሩ ነበሩ።
እንዲህ ዓይነት ብርቱ ሽማግሌዎችን ማጣት ጉዳቱ ለሀገር ነው። ፈጣሪ ነፍሳቸውን ይቀበላት።
አሚጎስ 145 ሚሊዮን ብር ማትረፉን አስታወቀ
አሚጎስ የገንዘብ ቁጠባና ብድር የህብረት ሥራ ማህበር፣ በ2016 በጀት ዓመት 145 ሚሊዮን ብር ባጠቃላይ ማትረፉንና ከ101 ሚሊዮን ብር በላይ የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን አስታወቀ፡፡ የማህበሩ አባላት የትርፍ ክፍፍል ድርሻ 53 በመቶ ነው ተብሏል፡፡
አሚጎስ ይህን ያስታወቀው ባለፈው ቅዳሜ ታሕሳስ 19 ቀን 2017 ዓ.ም፣ 11ኛ የባለአክስዮኖች ዓመታዊ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን በኢንተር ላግዠሪ ሆቴል ባካሄደበት ወቅት ነው፡፡
ለግማሽ ቀን በተካሄደው በዚህ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ የ2016 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻፀም ሪፖርት የቀረበ ሲሆን፤ በበጀት ዓመቱ ማህበሩ 145 ሚ ብር ማትረፉንና ከ101 ሚ. ብር በላይ የተጣራ ትርፍ ማግኘቱ ተነግሯል፡፡ የማህበሩ ጠቅላላ ሃብቱም 3 ቢሊዮን ብር ደርሷል ተብሏል፡፡
ተደራሽነትንና የአባላት የአገልግሎት አሰጣጥ እርካታን ለመጨመር አሚጎስ የቅርንጫፍ ቢሮዎችን በማብዛት፣ለአባላት ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት መስጠት እንዲቻል ጥናቶችን እያካሄደ እንደሚገኝ ተገልጿል። ማህበሩ፣ በተለያዩ ሀገራት እያደረጋቸው ያሉ የልምድ ልውውጦችና የስራ እንቅስቃሴዎችን በተመለከተም ገለፃ ተደርጓል፡፡
በተያያዘ ዜና፣ አሚጎስ የ12ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን በተለያዩ ኹነቶች ባለፈው ቅዳሜ ያከበረ ሲሆን፤ ለስኬታማ የማህበሩ አባላት የዋንጫ ሽልማትና ዕውቅና ተሰጥቷል፡፡ በኢንተር ላግዠሪ ሆቴል በተከበረው የማህበሩ የ12ኛ ዓመት የምስረታ ክብረ በዓል ላይ የኢትዮጵያ ህብረት ስራ ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባሳደር ሽፈራው ሽጉጤ፣ ምክትል ኮሚሽነር አቶ አብዲ ሙሃድ እንዲሁም የአዲስ አበባ ህብረት ሥራ ኮሚሽን ኮሚሽነር ወ/ሮ ልዕልት ግደይ በክብር እንግድነት ተገኝተዋል፡፡
በዚህ ክብረ በዓል ላይ የሕብረት ስራ ማህበሩን በትጋት ሲያገለግሉ ለቆዩት የአሚጎስ ሥራ አስኪያጅ አቶ ፍፁም አብርሃ፣ የኢትዮጵያ ህብረት ስራ ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባሳደር ሽፈራው ሽጉጤ ሽልማት አበርክተውላቸዋል፡፡ በተመሳሳይ፣ በአግባቡ በመቆጠብና በመበደር ለሌሎች የማህበሩ አባላት አርአያ የሆኑ ስኬታማ አባላትም የዋንጫ ሽልማትና ዕውቅና ተሰጥቷቸዋል፡፡
የዛሬ 12 ዓመት በሦስት ዓይን ገላጭ መሥራቾች ተጠንስሶ ዛሬ ወደ 10ሺ የሚጠጉ አባላትን ያፈራው አሚጎስ የህብረት ሥራ ማህበር፤ከ120 በላይ ሰራተኞችን ይዞ በተለያዩ የክልል ከተሞች ቅርንጫፎቹን በማብዛት ተደራሽነቱን እያሰፋ ይገኛል ተብሏል፡፡
የ”ወሰን ይገባኛል” ውዝግብ የዜጎችን ሕይወት ቀጠፈ
በሲዳማ ክልል እና ወላይታ ዞን መካከል የተፈጠረው የ”ወሰን ይገባኛል” ውዝግብ የዜጎችን ሕይወት ቀጥፏል። መንግስት ለዚህ ውዝግብ አፋጣኝ መፍትሔ እንዲሰጥ ተጠይቋል።
በወላይታ ዞን፣ አበላ አባያ ወረዳ፣ “አባያ ክላስተር” በሚባል የእርሻ ልማት ላይ “ከሲዳማ ክልል መጡ” የተባሉ የልዩ ሃይል እና ሚሊሻ አባላት ባለፈው ሐሙስ ታህሳስ 17 ቀን 2017 ዓ.ም. ጥቃት መፈጸማቸውን አንድ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የአካባቢው ነዋሪ ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል። ነዋሪው አክለውም፣ በሲዳማ ክልል እና ወላይታ ዞን መካከል የተከሰተው የ”ወሰን ይገባኛል” ውዝግብ መፍትሔ አለመበጀቱ በአካባቢው ላይ ውጥረት እንዲፈጠር እና ለዜጎች ሕይወት መቀጠፍ ምክንያት መሆኑን ገልጸዋል።
የእርሻ ልማቱ በመንግስት ሲተዳደር ቆይቶ፣ ኋላ ላይ “አሚባራ” በተሰኘ ድርጅት በኪራይ ሲለማ እንደነበር ያወሱት ነዋሪው፣ እርሻው የነበረበትን ዕዳ በመክፈል የወላይታ ልማት ማሕበር ላለፉት አራት ዓመታት በባለቤትነት እንደያዘው አብራርተዋል። ነዋሪው አክለውም፤ “ለእርሻው ከብላቴ ውሃ የሚያስተላልፈው ትልቅ ቱቦ በመሰበሩ ሳቢያ ውሃው ፈስሶ እርሻውን አበላሽቶ ለሁለት ዓመታት ያህል ስራ ቆሞ ነበር። ዘንድሮ ግን የልማት ማሕበሩ የራሱን ባለሞያዎችና ትራክተር በመያዝ ዳግም ለማልማት ወደ እርሻው አመራ።” ይላሉ።
ይሁንና ታህሳስ 17 ቀን 2017 ዓ.ም. ትራክተር በመያዝ ወደ ስፍራው የተጓዙት ባለሞያዎች ላይ “ከሲዳማ ክልል መጡ” የተባሉ የልዩ ሃይል እና ሚሊሻ አባላት ጥቃት ማድረሳቸውን የተናገሩት ነዋሪው፤ “የጥቃቱ መነሻ ምክንያት የእርሻውን ስፍራ ወደ ሲዳማ ክልል ለማካለል ነው” በማለት ነው። የአበላ አበያ ወረዳ ጥቃት ወደ ተፈጸመበት ስፍራ የፖሊስ ሃይል ቢያሰማራም፣ ሁኔታም “ከአቅሙ በላይ” እንደሆነበት ነዋሪው ይገልጻሉ። ከተላከው የፖሊስ ሃይል ጋር አብረው በተጓዙት የወረዳው አመራሮች እና የወላይታ ልማት ማሕበር ስራ አስኪያጅ ላይ እነዚሁ የልዩ ሃይሎች ጥቃት እንዳደረሱ የሚናገሩት ነዋሪው፣ ነገር ግን ጉዳት ሳይደርስባቸው ከስፍራው መሸሻቸውን ይጠቅሳሉ። ሆኖም ግን ሁለት ወጣቶች ተገድለው፣ ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ በርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች ደግሞ ቆስለው ሆስፒታል መግባታቸውን አመልክተዋል።
ነዋሪው በ1994 ዓ.ም. ተመሳሳይ ጥቃት ተፈጽሞ እንደነበር ያወሱ ሲሆን፣ በጥቃቱም በርካታ መኖሪያ ቤቶች እንደተቃጠሉና በንጹሃን ዜጎች ላይ ግድያ መፈጸሙን ይገልጻሉ። “ያኔም ሆነ አሁን የሲዳማ እና ወላይታ አካባቢዎችን የሚለይ ግልጽ ወሰን አለመኖሩ የችግር መንስዔ ነው። ወሰኑን ለመለየት ባለመቻሉ ችግሩ ተባብሶ ቀጥሏል። በዚያ ላይ ጥቃት ፈጻሚዎች ላይ መንግስት ሕጋዊ እርምጃ እየወሰደ አይደለም።” ብለዋል፣ ነዋሪው።የአገር መከላከያ ሰራዊት ጥቃት ከደረሰ በኋላ ዘግይቶ ወደ አካባቢው መግባቱንና ለነዋሪዎቹ በቂ ጥበቃ እያደረገ አለመሆኑን ያስረዱት እኚሁ ነዋሪ፣ “በነዋሪዎች ላይ ድብደባና ወከባ እየፈጸመ ነው።” ሲሉ ስሞታቸውን አቅርበዋል።
“የአካባቢው ሕዝብ ለወላይታ ዞን አስተዳደር በተደጋጋሚ ቅሬታ አቅርቧል። ነገር ግን የሕዝቡ ቅሬታ ሰሚ አላገኘም።” ያሉት ነዋሪው፣ አካባቢው በውጥረት ውስጥ እንደሚገኝና ሕዝቡ የደህንነት ስጋት እንዳለበት አያይዘው አመልክተዋል።
በጉዳዩ ዙሪያ የአበላ አባያ ወረዳ እና የሲዳማ ክልል የመንግስት ሃላፊዎችን አስተያየት ለማካተት ያደረግነው ጥረት ለጊዜው አልተሳካም።
ኃይሌ ሆቴልና ሪዞርት ጅማ በይፋ ተከፍቷል
አስረኛው ኃይሌ ሆቴልና ሪዞርት ጅማ፣ ባለፈው ሐሙስ ታህሳስ 24 ቀን 2017 ዓ.ም በጅማ ተመርቆ ተከፈተ፡፡ ባለ 4 ኮከቡ ኃይሌ ሆቴልና ሪዞርት ጅማ፤ የተለያዩ ዘመናዊ አገልግሎቶች የተሟሉላቸው 105 የመኝታ ክፍሎች ያሉት ሲሆን፤ የቪአይፒ አገልግሎት የሚሰጡና እያንዳንዳቸው አራት ክፍል ያላቸው ሁለት ቪላዎች፣ 5 የኦዲዮቪዥዋል መሳሪያዎች የተገጠሙላቸው የስብሰባ አዳራሾች አሉት፡፡ ሆቴልና ሪዞርቱ አራት ባህላዊና ዘመናዊ ምግቦችን የሚያቀርቡ ሬስቶራንቶች፣ለመዝናናትም ሆነ ጤንነትን ለመጠበቅ የሚያስችሉ የአዋቂና የህፃናት የመዋኛ ገንዳዎች ያሉት ሲሆን ጂምናዚየም፣ ስፓና ስቲም ባዝ፣ ሳውና ባዝና ሞሮኮ ባዝ ተሟልቶለታል፡፡ በይቻላል መርሁ የሚታወቀው አትሌት ሻለቃ ኃይሌ ገብረስላሴ የወላይታውን ኃይሌ ሆቴልና ሪዞርት ባስመረቀ በ10ኛ ወሩ የጅማውን ያስመረቀ ሲሆን፤ “ይህም በአንድ ዓመት ከአምስት ወር አንድ ሆቴል ለመገንባት የገባነውን ቃል ማክበራችንን ያሳያል” ብሏል፡፡ በምርቃት ሥነስርዓቱ ላይ የተገኙት የጅማ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ቲጃኒ ናስር ባደረጉት ንግግር፤ “ጥንታዊቷና ታሪካዊቷ ጅማ የበለጠ እንድትፈለግና የቱሪስት መዳረሻ እንድትሆን ሻለቃ ኃይሌ ትልቅ ስራ ሰርቶልናል፤ እኛም በሕይወት እስካለን የጅማን ሰላም እንጠብቃለን” ሲሉ በሆቴሉ ግንባታ የተሰማቸውን ደስታ ገልፀዋል።ከሁለት ዓመት ባነሰ ጊዜ ውስጥ ግንባታው መጠናቀቁ የተነገረለት ኃይሌ ሆቴልና ሪዞርት ጅማ፤ 1.7 ቢሊዮን ብር ፈጅቷል ተብሏል፡፡ ኃይሌ ሆቴልና ሪዞርት ጅማ በአሁኑ ወቅት ለ210 ቋሚ ሰራተኞች የሥራ እድል የፈጠረ ሲሆን፤ በሙሉ አቅሙ ስራ ሲጀምር የሰራተኞቹን ቁጥር ወደ 400 እንደሚያሳድግ ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ አቶ ጋዲሳ ግርማ ገልጸዋል። ኃይሌ ሆቴሎችና ሪዞርቶች በቅርቡ የሻሸመኔውንና የደብረብርሃን ከተማ መዳረሻውን ለማስመረቅና ሥራ ለማስጀመር ቀን ከሌት እየሰራ መሆኑንም አቶ ጋዲሳ ግርማ ተናግረዋል። ኃይሌ ሆቴልና ሪዞርት ቀጣይ መዳረሻውን ወደ ምስራቅ ኢትዮጵያ በማዞር፣ በድሬደዋና በሐረር አድርጎ፣ በዚያው ወደ ጎረቤት አገር የመሻገር እቅድ እንዳለውም ተጠቁሟል፡፡የሃዋሳው ኃይሌ ሆቴልና ሪዞርት እንዲገነባ መሬት በመፍቀድ ከ24 ዓመት በፊት አስተዋፅኦ ያደረጉት የቀድሞው የደቡብ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አባተ ኪሾ በምርቃቱ ላይ በክብር እንግድነት ታድመዋል፡፡
የ25 ዓመት ረዥም ጉዞ የተጀመረው በዚህ ነው!!
የ25 ዓመት ረዥም ጉዞ የተጀመረው በዚህ ነው!!
ውድ የአዲስ አድማስ ቤተሰቦች፡- የመጀመሪያው አዲስ አድማስ ጋዜጣ ታትሞ ለንባብ የበቃው ታህሳስ 29 ቀን 1992 ዓ.ም ነበር - የዛሬ 25 ዓመት በዕለተ ቅዳሜ፡፡ ከዚያን ጊዜ አንስቶ ያለ አንድ ቅዳሜ በስተቀር ጋዜጣው ያልወጣበት ቀን የለም፡፡ እሱም ቢሆን የተከሰተው በ97 ምርጫ ማግስት በተከሰተው ፖለቲካዊ ቀውስ ሳቢያ ነበር፡፡
የዛሬ 20 ዓመት፣ የአዲስ አድማስ ጠንሳሽ፣ መሥራችና ባለቤት አሰፋ ጎሳዬ (አሴ) በድንገተኛ ህመም ህይወቱ ባለፈበት ወቅት እንኳን ጋዜጣው ሳይታተም አልቀረም፡፡ ረቡዕ ከቀብር በኋላ ቢሮ ገብተን የቅዳሜውን ጋዜጣ ስናዘጋጅ ትዝ ይለኛል፡፡ እያነባንም ቢሆን የቅዳሜውን ሳምንታዊ ጋዜጣ በጉጉት ለሚጠብቀን ውድ አንባቢ አድርሰናል፡፡
አሁን ሳስበው ታዲያ ያኔ ትክክለኛ ሥራ ነው የሰራነው፡፡ የአሴ ነፍስ በዚያ ተግባራችን ጮቤ እንደረገጠች አልጠራጠርም፡፡ እርሱ በህይወት ባይኖርም አዲስ አድማስ መታተሟ፣ ህልምና ራዕዩን ማስቀጠያ ብቸኛ መንገድ ነበር፡፡
እነሆ ከዚያም በኋላ ሁለት አሰርት ዓመታትን አስቆጥራ፣ በብዙ ውጣ ውረዶችና ተግዳሮቶች አልፍ እነሆ ለ25ኛ ዓመቷ በቅታለች፡፡ በግሉ ፕሬስ ሩብ ክፍለዘመን ቀላል ጊዜ አይደለም፡፡ ቀላል ዕድሜ አይደለም፡፡ የ25 ዓመት ጉዞ ሀ ብሎ የተጀመረው ግን በዚህ ነው፡፡ ታህሳስ 29 ቀን 1992 ዓ.ም በታተመችው አዲስ አድማሰ ጋዜጣ፡፡
እንኳን አደረሳችሁ፤ አደረሰን!!
ወቅታዊው የጸጥታ መደፍረስና የኑሮ ውድነት ፈተና እንደሆኑበት ዝግባ የሕጻናትና አረጋውያን መርጃ የበጎ አድራጎት ድርጅት አስታወቀ
ከተመሰረተ 16 ዓመታትን ያስቆጠረው ዝግባ የሕጻናትና አረጋውያን መርጃ የበጎ አድራጎት ድርጅት፤ በአማራ ክልል የተፈጠረው የጸጥታ መደፍረስና የኑሮ ውድነት ፈተና እንደሆኑበት አስታውቋል። ድርጅቱ የምስረታ ክብረ በዓሉን ለማክበር በዝግጅት ላይ መሆኑንም ገልጿል።
ባለፈው ሐሙስ ታህሳስ 24 ቀን 2017 ዓ.ም. በጌትፋም ሆቴል በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የድርጅቱ ሃላፊዎችና የበጎ ፈቃድ አምባሳደሮች የተገኙ ሲሆን፣ ስለድርጅቱ ዝርዝር ማብራሪያ አቅርበዋል። በማብራሪያቸውም ላይ ድርጅቱ ዋና መቀመጫውን በባሕር ዳር ከተማ በማድረግ ከ2 ሺሕ 650 በላይ ወላጆቻቸውን በሞት ላጡና ለከፋ ችግር የተጋለጡ ሕፃናትና ጧሪ አልባ የሆኑ አረጋውያን በመደገፍ፣ እንዲሁም ችግረኛ ሴቶችን በገቢ ማስገኛ ስራ በማሰማራት ኑሯቸውን እንዲያደላድሉ ማስቻሉን የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ስለሺ ጌታቸው አመልክተዋል።
በ27 በጎ ፈቃደኛ ግለሰቦች የተቋቋመው ይህ የበጎ አድራጎት ድርጀት፣ የራሱ ተሽከረካሪዎች እንደሌሉት፤ የቦታ ጥበት እንዳለበት፤ የከርሰ ምድር ውሃ ችግር ስለመኖሩ በዚሁ መግለጫ ተነግሯል። ከዚህም ባለፈ በአማራ ክልል የተፈጠረውን የጸጥታ መደፍረስና የኑሮ ውድነቱን ተከትሎ፣ የተፈጠረው የፍጆታ ዕቃዎች አቅርቦት ዕጥረት "እየፈተነኝ ነው" ሲል ድርጅቱ አስረድቷል።
"ለአካል ጉዳተኞች እና ዕድሜያቸው ለገፋ ሰዎች የሚያገልግል ዊልቸር ዕጥረት ተፈጥሮብኛል" ያለው ድርጅቱ፣ በጎ ፈቃደኛ የሆኑ ግለሰቦች፤ በተለይም ከዚህ ቀደም ድጋፍ ለማድረግ ቃል የገቡ ባለሃብቶች ቃላቸውን ተግባር ላይ እንዲያውሉ ጠይቋል። የድርጅቱ የገቢ ምንጭ በአብዛኛው ከአባሎች በሚገኝ መዋጮ፣ በድርጅቱ ስር ካለው ትምሕርት ቤት እና በባሕር ዳር ከተማ ከከፈተው የፍራፍሬ ጭማቂ መሸጫ ቤት የሚመነጭ በመሆኑ፣ በስሩ ለሚገኙ 50 ቋሚ ሰራተኞች ደመወዝ ከመክፈል እና በማዕከሉ ላሉ ድጋፍ የሚሹ ወገኖች ድጋፍ ከማድረግ በዘለለ መጠነ ሰፊ ስራዎችን እንዳይሰራ ተግዳሮት እንደሆኑበት ጠቁሟል።
ዝግባ የሕጻናትና አረጋውያን መርጃ የበጎ አድራጎት ድርጅት 16ኛ ዓመት የምስረታ ክብረ በዓሉን ለማክበር መዘጋጀቱን በመጠቆም፣ ገቢ ከማሰባሰብ በተጨማሪ የመገናኛ ብዙሃን ትኩረታቸውን ለድርጅቱ እንዲያውሉ ዕንቅስቃሴ እንደሚያደርግ አብራርቷል።
ዓለምፍሬ ፒንክሃውስ ካንሰር ፋውንዴሽን የድጋፍ ጥሪ አቀረበ
ዓለምፍሬ ፒንክሃውስ ካንሰር ፋውንዴሽን ለመላ ኢትዮጵያውያን የድጋፍ ጥሪ አቅርቧል። ፋውንዴሽኑ በተደጋጋሚ የመሬት ጥያቄ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጥያቄ ቢያቀርብም፣ ምላሽ እንዳላገኘ አመልክቷል።
ባለፈው ዓርብ ታሕሳስ 25 ቀን 2017 ዓ.ም. በግዮን ሆቴል ሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ፋውንዴሽኑ በዶክተር ፍሬሕይወት ደርሶ ከአስራ ሶስት ዓመታት በፊት በአሜሪካ አትላንታ እንደተመሰረተ በማውሳት፣ በካንሰር ሕመም ላይ ቅድመ መከላከል የግንዛቤ መስጠት ስራ ሲሰራ መቆየቱ ተብራርቷል። በአዲስ አበባ እና ጎንደር ከተሞች ከ8 ሺሕ በላይ የካንሰር ታማሚዎችን የሕክምና አገልግሎት እንዲያገኙ እያደረገ የሚገኝ ድርጅት መሆኑም ተገልጿል።
የድርጅቱ የቦርድ አባል ወይዘሮ ጸዳለ ጽጌ እንዳስታወቁት፣ ፋውንዴሽኑ በዓመት ሁለት ጊዜ በካንሰር ሕመም ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጫ ኮንፈረንስ ያዘጋጃል። አክለውም፣ በሁለተኛው ኮንፈረንስ አማካይነት በሕመሙ የተጠቁ ወገኖች እርስ በርሳቸው የውይይት መድረክ እንደሚያካሂዱ አስረድተዋል።
"የካንሰር ታማሚዎች ጤና የእርስዎም፣ የእኔም፣ የሁላችንም ጉዳይ ነው" የሚለው ፋውንዴሽኑ፣ መላ ኢትዮጵያውያን የድጋፍ እጃቸውን እንዲዘረጉ ጠይቋል። አሁን ላይ እየሰራቸው ካሉ ስራዎች በተጨማሪ፣ በቀጣይ ሌሎች በርካታ ዕንቅስቃሴዎችን ለማድረግ የተለያዩ ዕቅዶችን እንደነደፈ ተነግሯል።