Administrator

Administrator

•  በ4 ወራት ውስጥ ከ15 ሺ በላይ ቤት ፈላጊዎችን መዝግቧል


በአራት ወራት ውስጥ 15 ሺህ 388 ቤት ፈላጊዎችን መመዝገቡን ያስታወቀው  ኪ  ሀውሲንግ ፋይናንስ ሶልሽን፤ በዛሬው ዕለት ከ6 ሰዓት ጀምሮ በዲ ሊኦፖል ሆቴል ባካሄደው ዕጣ የማውጣት ሥነሥርዓት 60 ቤት ፈላጊዎችን የቤት ባለቤት አድርጓል፡፡

በዕጣ ከወጡት 60 አፓርተመንት ቤቶች  ውስጥ ሰላሳው ባለ ሦስት መኝታ  ክፍል፣ ሃያ አንዱ ባለሁለት  መኝታ ክፍል ሲሆኑ፤ ዘጠኙ ደግሞ ደግሞ ባለ አንድ መኝታ ክፍል መሆናቸው ተነግሯል፡፡

ዕጣ የወጣላቸው አፓርትመንቶች በፒያሳ፣ በጋርመንትና  በሀያት የሚገኙ ሲሆኑ፤ ሙሉ ለሙሉ ግንባታቸዉ ያለቀላቸው መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ኪ ሀውሲንግ፤ በአስር አመት ውስጥ እስከ 100 ሺህ የሚደርሱ ቤቶችን ገንብቶ ለቤት ፈላጊዎች ለማስረከብ ዕቅድ እንዳለው  አስታውቋል።

ኪ ሃውሲንግ ፋይናንስ ሶሉሽን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር፣ ባለፈው ነሀሴ ወር የመኖሪያ ቤት ፈላጊዎች በ77 ሺ 280 ብር ቅድመ ቁጠባ የቤት ባለቤት የሚሆኑበትን ሞዴል ፕሮጀክት ማስተዋወቁ አይዘነጋም፡፡

Thursday, 04 January 2024 00:00

“የእኔ ሽበት”

“የእኔ ሽበት” እና ሌሎች ግጥሞች” በተሰኘ ርዕስ  በመጽሐፍ ያሳተመው፡፡ የወላለዬ ወለቶት ከያዟቸው ምሥጢራት ባሻገር የመጽሐፉ ዲዛይን፣ መልክአ ፊደል እና ኅትመቱ በዓይነቱ ልዩ የሚባል ነው፡፡ በጃፋር መጽሐፍት ያገኙታል፡፡

“ሆኖ መገኘት” የተሰኘው በሻለቃ ኃይሌ ገ/ስላሴ የህይወት መርሆች እና በሚያስተዳድራቸው ሆቴሎች መነሻ ተደርጎ በአቶ መልካሙ መኮንን እና በአቶ ፋሲል መንግስቴ በጋራ የተዘጋጀው መፅሀፍ በዛሬው እለት በሀይሌ ግራንድ ሆቴል ሻለቃ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው የክብር እንግዶች በተገኙበት ተመርቋል፡፡
በመፅሐፉ ምረቃ ላይ የመፅሃፉ ፀሀፊ ከሆኑት እንዱ አቶ መልካሙ መኮንን እንደገለጹት የመፅሃፉ ዋና ዋና አላማዎች እያንዳንዳችንን ለስኬት የሚያበቁ እና ሊኖሩን የሚገቡ መርሆዎች እና ባህርያትን በተግባር ከተፈተነው ከሻለቃ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ የሀይወት ተሞክሮ የተቀዱና ተሰናድተው የቀረቡ የስኬት ሚስጥራትን ለአንባቢያን ማድረስ እንደሆነ ተናግረዋል
እንዲሁም መፅሐፉ የላቀ አገልግሎት አሰጣጥ ባህልን በድርጅት ውስጥ ማስረፅ ወይም መገንባት ለድርጅት ዘላቂነት እና ተወዳዳሪነት ዋነኛ መንገድ እንደሆነ ማሳየት ሌላኛው አላማው እንደሆነም ሌላኛው የመፅሃፉ ፀሀፊ አቶ ፋሲል መንግስቴ ገልጸዋል
መፅሀፉን ለአንባቢያን ለማብቃት ከ1 አመት በላይ እንደፈጀ መፅሀፉ ላይ በድርሰት የተሳፉት አቶ ደሳለኝ ስዩም የገለፁ ሲሆን ሻለቃ ኃይሌ ገ/ስላሴ የመፅሃፉ ደራስያን ና አዘጋጆች ይህን አስተማሪና አነቃቂ መፅሀፍ ለአንባቢያን በማዘጋጀታቸው ያለውን ትልቅ ምስጋናውን ገልጿል

 የገና ትውስታ-የዛሬ 24ዓመት


        “በነቢያት ጥሪ መሰረት እጅ መንሻ እንዲያቀርቡ የተጠሩት ኢትዮጵያውያን ናቸው” ሲሉ አለቃ አያሌው ገለፁ፡፡
ትክክለኛው የዘመን አቆጣጠርም የኢትዮጵያውያን መሆኑን አስታወቁ፡፡
ከብሉይ ኪዳን መፃህፍት የተለያዩ ምዕራፎች አስረጅ እየጠቀሱ እጅ መንሻ እንዲያቀርቡ የተጠሩት ኢትዮጵያውያን ናቸው የሚሉት አለቃ አያሌው፤ “ኢትዮጵያውያን የትንቢት ጥሪ፣ የትንቢት ቀጠሮ አላቸው፡፡ ይህን ትንቢት ሲጠብቁ ኖሩ፡፡ ጊዜው ደረሰ፡፡ ኮከብም ወጣ፡፡ አምላክ ተወለደ፡፡
 በኮከብም እየተመሩ ሄደው መባዕ ይዘው ሰግደውለታል፡፡ ይህን ያደረጉት ኢትዮጵያውያን ናቸው፡፡” ብለዋል፡፡
 አክለውም፤ “ከክርስቶስ ልደት ቀደም ሲል የኢትዮጵያውያን አባት የሚባለው ታላቁ ፈላስፋ ዥረ ጀሽት ይኸው ትንቢት ተገልፆለት ድንግል ህፃኗን እንደታቀፈች የሚያሳይ ምስል ክብረት ቀርፆ ነበር” ሲሉ አለቃ አያሌው አብራርተዋል፡፡በመቀጠልም፤ በውሃ ዳር ተቀምጦ ክዋክብትን ሲመረምር ማሪያም ልጇን እንደታቀፈች በኮከብ ላይ ታትሞ በማየቱ ትንቢቱ ተገልጦለት፣ “የሚወለደው የሰላም አባት ስለሆነ ሄዳችሁ ስገዱለት” ብሎ ማዘዙንና በዚሁ መሰረት ኢትዮጵያውያኑ በኮከብ እየተመሩ ወደ ቤተልሄም እንደ ሄዱ አለቃ አያሌው ይናገራሉ፡፡
ከዚህም ጋር በማያያዝ፣ ግርጎሪ የተባለው ሊቀ ጳጳሳት የቀመረው የዘመን አቆጣጠር የተሳሳተ መሆኑን አብራርተው፤ “እንኳን ለአውሮፓውያን ለአይሁድም የክርስቶስን መወለድ የነገሯቸው ኢትዮጵያውያን ናቸው” ያሉት አለቃ አያሌው፤  “ኢትዮጵያውያ ለአምላክ ምስክር ናቸውና ከነሱ የበለጠ ሊጠየቅ የሚገባው የለም” ብለዋል፡፡
ኢትዮጵውያን የዘመን አቆጣጠራቸው የተፋለሰው ክርስቶስ ከተወለደ ከ8 ዓመት በኋላ ዘግይተው ስለሰሙ ነው” የሚለውን አስታውሰው፣ “ይህ የፌዘኞች አባባል ነው፡፡ መጠየቅ የሚገባቸውስ ኢትዮጵያዊያን ናቸው፡፡ አይሁድ እያወቁት አልተቀበሉትም፡፡ አውሮፓውያንም አያውቁትም፡፡ ክርስቶስን ስለማያውቁ ቢጠይቁ ነውር የለውም፡፡ ለዕውቀቱ ደግሞ ኢትዮጵያዊያን ናቸው መሰረቶቹ” ሲሉ ገልፀዋል፡፡
ምንጭ፡- (አዲስ አድማስ ጋዜጣ፤ ነሃሴ 28 ቀን 1992፤ የመጀመሪያው ዕትም)

ትንታጉ ጋዜጠኛ ደረጀ ኃይሌ ኬንያ ናይሮቢ ተሻግሮ ከቀድሞው አወዛጋቢ አክቲቪስትና ፖለቲከኛ ጃዋር መሃመድ ጋር ያደረገውን ቃለመጠይቅ አርት ቲቪ አቅርቦልናል፡፡ ጋዜጠኛው በቃለ መጠይቁ እንደለፀው ሰሞኑን ያየነው ጃዋር ድሮ የምናውቀው አይደለም፤ ግንፍል ግንፍል የሚለው ጃዋር አልተገኘም፡፡ እንደ ጎረምሳ እምቡር እምቡር የሚለው ጃዋር የለም፡፡ የረጋ - የሰከነ - የሰላ - የበሰለ አዲስ ጃዋር ነው የተዋወቅነው፡፡  ከእስር ከተፈታ በኋላ ድምፁ የጠፋው (ያለበትም ጭምር)  ጃዋር መሃመድ፤ ድንገት ለአገሩ የሚቆረቆር፣ ለህዝቡ የሚያስብና የሚጨነቅ፣ ሰላምን አጥብቆ የሚሰብክ፣ ወቀሳና ትችት ከመሰንዘር ይልቅ ሃሳቦችና ምክሮች ማቅረበ  የሚቀናው ሆኖ ነው ያገኘነው፡፡ በተለይ ደግሞ ጦርነትን ደጋግሞ ሲነቅፍ ሰምተናል (ሁላችንም መንቀፍ አለብን)፡፡ ከግጭት ይልቅ ምክክርን፣ ውይይትን ድርድርን ደጋግሞ መክሯል፡፡
ለኢትዮጵያ ሰላምን - ብልፅግናን - ዲሞክራሲን እኩልነትን ወዘተ (በጎ በጎውን) የሚመኝና የሚሻ ሆኖ ነው ያገኘነው - በጋዜጠኛ ደረጀ ሃይሌ ቃለ መጠይቅ፡፡  
አንዳንዶች “ሲያስመስል” ነው የሚል አስተያየት ቢኖራቸውም፣ ማስረጃ ወይም ማረጋገጫ ግን አያቀርቡም፡፡
 በይፋ ከፖለቲካው ሜዳ መውጣቱን ከተናገረ በኋላ የሚያስመስልበት ምክንያት ብዙም አያሳምንም፡፡ የሆኖ ሆኖ፣ ከዚህ ቃለመጠይቅ ጋር በተያያዘ የደረስኩበትን የጥናት ውጤት የሚመስል ግኝት ልንገራችሁ፡፡ አንደኛ፤ ኢትዮጵያውያን (ከሊቅ እስከ ደቂቅ) ትንሽ በጎ ነገር ካየ ይቅርታ ሳይጠየቁ ይቅርታ የሚያደርግ ጨዋ ህዝብ ነው - በፍጥነት ተበደልኩ የሚለውን የሚረሳ፡፡ ጃዋር ከመታሰሩ በፊት በሚሰጣቸው ቃለመጠይቆችና አስተያየቶች ላይ መሳ ለመሳ ድጋፍና ነቀፌታ የሚጎርፍለት ፖለቲከኛ ነበር፡፡ በአማርኛ በሚሰጣቸው ቃለ መጠይቆች ከድጋፍ ይልቅ ነቀፌታ ይበዛበት ነበር፡፡ ይሄ ደግሞ በአብዛኛው ከራሱ ንግግር ወይም አንደበት አሊያም ሃሳብ ምክንያት ተንኳሽነት የሚመጣ ይመስለኛል ነበር፡፡ እሱና የፖለቲካ ባልደረቦቹ (“የአማራ ኢሊቶች”) የሚሏቸው ላይ በሚሰነዝሯቸው የሚያስቆጡ ፍረጃዎችና አስተያየቶች የተነሳ አያሌ የሚነቅፉትና የሚቃወሙት ቢፈለፈሉ አይደንቅም፡፡ የሆነውም እንደዚያ ነው፡፡ በዚህም የተነሳ ዲጂታል ሚዲያ ላይ እሱ በተናገረ ቁጥር የስድብና ዘለፋ ዶፍ ይወርድበታል (በአብዛኛው ጨዋነት የጎደላቸው)፡፡ ግን ምንም ላይመስለው ይችላል፡፡ አላማው የድጋፍ መሰረቱን ማስደሰት ነው፡፡ እነሱ ያሞግሱታል ሌላው ደግሞ ጭራቅ አድርጎ የእርግማን መዓት ያወርድበታል፡፡
ይሄ ግን በጃዋር ላይ ብቻ የሚከሰት ልዩ ነገር አይደለም፡፡ በሁሉም የኢትዩጵያ ፖለቲከኞች ላይ የተለመደ ነው በተለይ ፅንፈኛ የብሄር ፖለቲካ በሚያራምዱት ላይ ይብሳል፡፡ ባለፈው እሁድ በአርት ቲቪ ቀርቦ ዩቲዩብ የተለቀቀው የጃዋርና የጋዜጠኛ ደረጀ ክፍል አንድ ቃለ መጠይቅው በ24 ሰዓት ውስጥ 1 ሚሊዮን ሰው አይቶታል - እስካሁን በዘፈንም ድራማም ከተመዘገበው ሪከርድ ሳይበልጥ አይቀርም፡፡ እኔን ግን ከተመልካቹም በላይ የገረመኝ ጃዋር የተሰጡት አስተያየቶች ናቸው ኮሜንቶች ዓይነት ነው፡፡ በርካታ አጫጭርም ረዣዥምም አስተያየቶች ሰፍረዋል፡፡ በሚገርም ሁኔታ  አንድም ነቀፌታ፣ ትችት፣ (ቢያንስ እስከ ትላንት በስቲያ) አልገተመኝም ልብ አድርጉ የዘፈን ክሊፕ አይደለም የተለቀቀው ልብ አንጠልጣይ ፊልም ወይም ድራማ አይደለም፡፡ ከቀድሞ አወዛጋቢ ፖለቲከኛ (ደጋፊም ተቃዋሚም መሳ ለመሳ ያለው) ጋር የተደረገ ኢንተርቪው ነው - ወይም ወይይት በሉት፡፡ ሆኖም አድናቆት - ውደሳ - ምስጋና ማበረታቻ ያዘሉ አስተያየቶ ነው እኔን የገጠመኝ፡፡ ይሄ እንዴት ሊሆን ቻለ? ዝርዝር ማብራሪያ ያለው ምላሽ ለመስጠት ጥናት ይፈልጋል፡፡ እኔ ግን የተሰጡትን ኮሜንቶች ደጋግሜ ካነበብኩና በእንግሊዝኞቹን የተፃፉትን ክፍሎቹን ወደ አማርኛ ከመለስኩ በኋላ የደረስኩበት ድምዳሜ ሁለት ነው፡፡
አንድም ቃለ መጠይቁን የተከታተለው ሰው በቀድሞ አወዛጋቢ ፖለቲከኛ ጃዋር ድንገተኛ የባህርይ ለውጥ ደንግጧል - ጨርሶ ያልጠበቀው ሆኖበታል፡፡ አሊያም ደግሞ የጃዋር መረጋጋ - መስከን መብሰል እንዲሁም እነሱንም እንዲቆጠቡ እንዲረጋጉ አድርጓቸዋል፡፡ ከዩቲዩቡ ስር ከሰፈሩ ኮሜንቶች ሶስት ያህሉን ከዚህ በታች አቅርቤላችኋለሁ፡፡ ፖለቲከኛውም ደጋፊውም ከተረጋጋ አገር ትረጋጋለች፡፡
 “ዋው! ቃለመጠይቁ ዕፁብ ድንቅ ነው! የጃዋር ልባዊ የሰላም ጥሪ ከምር ልቤን ነክቶታል፡፡ ጠንካራና ጥልቅ ውይይት ነበር! ጃዋር፤ ስለ ሰላም ስለሰበክኸንና የራስህን አርበኝነት ስላሳየኸን እናመሰግናለን፡፡ ይህ ደግሞ ጠባብ አለመሆንህን ያረጋግጣል፡፡ ጋዜጠኛ ደረጀም ለውይይቱ ጥልቀትና ርቀት ወሳኝ፣ ደፋርና ወቅታዊ ጥያቄዎች በማንሳቱ እኩል ምስጋና ይገባዋል፡፡
“ለውጥ” ተብዬዉ ከመምጣቱ በፊት በኦሮሚያ አብዮት ወቅት፣ ጃዋርን እንደፅንፈኛና ለዚህች አገር እንደ አደጋ ነበር የማስበው፡፡ ሆኖም ወደ ኢትዮጵያ በተመለሰ ጊዜና የፖለቲካ አቋሙን ከፈተሽኩት በኋላ እይታዬ ተቀየረ፡፡ በሰሜኑ ጦርነት ወቅት የሰጠው ቃለመጠይቅ ኹነቶችን በትክክል የመተንበይ ብስለትና የፖለቲካ ልህቀትን አሳይቷል፡፡ ከጦርነቱ በኋላ ጃዋር፣ አስደናቂ እድገት ያሳየ ሲሆን ወደ ብስለትና ብልህነት አድጓል፡፡ ጋዜጠኛ ደረጀ ሃይሌ ግንዛቤ የሚያስጨብጡ ውይይቶች በጥበብ በማሳለጥ የጥራትና ሙያዊ ብቃትን ምንነትን አሳይቷል፡፡ ይህም በሚገባ የተዘጋጀ የተደራጀና ሥነምግባራዊ ጥረት የታከለበት ጋዜጠኝነት ምን እንደሚመስል ያሳያል፡፡ አርት ቲቪ እንደዚህ ያለ የሚበረታታ ፕሮግራም በማቅረብ  ለእንግዶች ጥልቅና ተስማሚ የሆነ መድረክ በማሰናዳቱ እናመሰግናለን፡፡ ቃለ መጠይቁ ግሩም ነበር የጋዜጠኝነት ብቃትን አጉልቶ ያሳየ፡፡ ሁለተኛውን ክፍል በጉጉት እጠብቃለሁ”
“ቃለ መጠይቁ በዩቲዩብ በተለቀቀ በ24 ሰዓት ውስጥ 1ሚ. እይታዎች አግኝቷል፡፡ ይህም ሰውየው (ጃዋርን ማለት ነው) ምን ያህል ተፅዕኖ ፈጣሪ እንደሆነ የሚያመለክት ነው፡፡ ብዙ ጊዜያቸውን ሳይንሱን በማጥናት ያሳለፉ ሃቀኛ ሰዎች ፖለቲካ ሲያወሩ መስማት ደስታ ይሰጣል፤ ቃላቶቻቸው ይማርካል”

ድምጻዊ ቴዎድሮስ አሰፋ (ቴዲ ዮ) ከዞጃክ ወርልድ ዋይድ ጋር በመተባበር ያዘጋጀውን  “ይለያል” የተሰኘ ሦስተኛ አልበሙን በትላንትናው ዕለት ለገበያ ማቅረቡ ታውቋል፡፡ ሦስተኛ አልበሙ መውጣቱን አስመልክቶ ድምጻዊው ከትላንት በስቲያ በማሪዮት ሆቴል ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ፤አልበሙ በአይቲውስ እና በአማዞን ከፊታችን ረቡዕ ጀምሮ በይፋ እንደሚለቀቅ ጠቁሞ፣ አዲሱ አልበም  10 ሙዚቃዎችን ማካተቱንና ሦስቱ የቪዲዮ ክሊፕ እንዳላቸው አመልክቷል፡፡ በዚህ አለም አቀፍ ጥራቱን የጠበቀ ነው በተባለለት የሙዚቃ አልበም ላይ በአጃቢነት ከተሳተፉ ታዋቂ ድምፃዊያን መካከል ሱራፌል ፣ ካስማሰ ፣ ቃል ኪዳን ፣ ኩል ሱሬ እና እዮቤድ ይገኙበታል ተብሏል፡፡ በቅንብርና በሚክሲንግ ቢግ ባድ ሳውንድ እንደተሳተፉበት ታውቋል፡፡


 በአይሁዳውያን የሚነገር የአንድ ብልጥ አይሁድ አፈታሪክ እንዲህ ይላል።
አንድ ጊዜ አንድ ህጻን ልጅ በአንድ አይሁዳውያን መንደር ሞቶ ይገኛል። የመንደሩ አይሁዳውያን ተጠሪ የግድያ ተጠርጣሪ ይሆንና ፍርድ ቤት ይቀርባል። ጥፋተኛ ሆኖ ከተገኘም እንዲቃጠል ይወሰናል።
ዳኛው አይሁዳውያንን አይወዱም። ስለዚህ በአደባባይ እንዲህ አሉ፤ ወደሰማይ እየተመለከቱ፤
“እንግዲህ ፍርድ የአምላክ ነው። ሁለት ወረቀቶች ላይ እጣ እጽፋለሁ። “ወንጀለኛ” እና “ከጥፋት ነጻ” አይሁዱ “ወንጀለኛ” የሚለውን ካወጣ እንዲቃጠል ተፈረደበት ማለት ነው። “ከጥፋት ነፃ” የሚል የሚለውን ካወጣን በነጻ ይለቀቃል ማለት ነው።” አሉ።
ዳኛው ይህን ካሉ በኋላ ግን በልባቸው አይሁዱ በምንም አይነት ነጻ የማይወጣበትን ዘዴ እየፈለጉ ነበር። ማንም እንደማይጠረጥራቸው እርግጠኛ ነበሩ። ያገኙት ዘዴ በሁለቱም እጣ ወረቀት ላይ “ወንጀለኛ” የሚል መጻፍ ነበር። ጻፉና ሳጥኑ ውስጥ ከተቱ።
አይሁዱ ወደ እጣ ማውጫው ሳጥን እንዲመጣ ተጠራ። አይሁዱ ግን ዳኛውን ጠርጥሯቸዋል። ስለዚህ እሱም በበኩሉ ዘዴ ሲያጠነጥን ቆይቶ ኖሯል።
ከሳጥኑ ውስጥ አንዱን የተጠቀለለ እጣ አውጣና ሳይገለጥ በፊት እንደተጠቀለለ ወደ አፉ ከተተና በፍጥነት አኝኮ ዋጠው።
ዳኛው አይናቸው ፈጠጠ። ደነገጡ።
“ይሄ ምን ማለት ነው? ምንድን ነው ነገሩ?” ሲሉ ጠየቁ።
“ነገሩ ቀላል ነው። ሳጥኑ ውስጥ የቀረውን እጣ በማየት ወንጀለኛ መሆን አለመሆኑን ማወቅ ይቻላል” ሲል  ሀሳቡን ገለጸ። የቀረው እጣ  ይታይ በሚለው ላይ ተስማሙ። በኋላም ሳጥኑ ውስጥ ያለው እጣ ወጣ። ተገልጦ ሲታይ “ወንጀለኛ” ይላል። ዳኛው “ይሄዋ ወንጀለኛ ነህ” አሉት።
አይሁዱ፤ “ወንጀለኛ አይደለሁም። ምክንያቱም ይሄ ማለት እኔ የዋጥኩት “ከጥፋት-ነጻ” የሚለውን እጣ ነው ማለት ነው። ስለሆነም መፈታት ይገባኛል” ሲል አብራራ። ዳኛው ምንም ሰበብ ፈጥረው ወንጀለኛ ሊደርጉት ባለመቻላቸው እንዲለቀቅ ወሰኑ።

ያላግባብና በጥላቻ “ጥፋተኛ ነህ” የመባል አደጋ ሊኖር እንደሚችል መጠራጠር ተገቢ ነው። በቀላሉ ለመገመት እንደሚቻለኝው፤ ማንም የባላንጣውን ትክክለኛ መልስ የማረጋገጥና አበጀህ የማለት ቀናነት የለውም። በተለይም ድክመቱን የሚያሳይ ገጽታውን አይፈልገውም።
ከስር መሰረቱ ጥፋቱን እንጂ ልማቱን የማይፈልጉ ባላንጣን ምንም ቀዳዳ ሊሰጡት አይሹም። ይልቁንም ህይወቱን አደጋ ላይ “ወንጀለኛ” ብሎ ጽፎ መገላገልን ይመርጣሉ።
አንዳንድ ጊዜ ንጹህና ሀቀኛ መሆን ብቻ ሳይሆን ብልህ መሆንን እንደሚያሻ መገንዘብ አስፈላጊ ነው። የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች ቢበዛ ብልህነት ቢያንስ ደግሞ ብልጠነት እንደሚያጡ ልብ ማት አለብን። በሁለቱም እጣ ወንጀለኛ ላለመሆን አንዱን በንጥሩ ለመጨበጥ የረባ እርምጃና አስተሳሰብ ያስፈልጋል። ለዚህ ደግሞ ያረጀ ልማድና የአመለካከት ዘዴን መለወጥ ዋና ጉዳይ ሆኗል። የምትበድለውን ማወቅ ከበቀሉ ያድንሃል። “አትዋልባት እንዳትውልብህ፣ አትሳላት እንዳታርድህ” እንዲል መጽሐፈ-ምሳሌያዊ አነጋገር። ጭፍን ጥላቻ በየትም መልኩ ቢመጣ የሀገራችን ጠላት ነው። ከኔ ካልሆንክ ከጠላቴነህ ላይ የከፋ ጽንፉ የመሆኑን ያህል ከእኔ ጋር ቆይተህ ድክመት ከታየብህም የጠላቴን ፖለቲካ አጠናክረሃል ማለትም ያው የተሳሳተ ድምዳሜ ነው። ዞሮ ዞሮ ከጠላት የመፈረጃ መካከለኛ ሞገድ ነው። በወጉ በመደራጀት በመብዛትና በመባዛት ፓርቲን ማጠናከር ዋና ነገር ነው። “አትጎብዙ ማለት ነው እንጅ እርግማን አትባዙስ እርግማን አይደለም” የሚለውን ተረት ልብ እንበል። “ጠንካራ ተቃዋሚ ይስጠን” ማለት ጥሩ ጸሎት ነው። ተቃዋሚ እንዳይጠናከር እንቅፋት መፍጠር ግን ከሃጥያት አንዱ ነው። ተቃዋሚው አልጠነክር ማለቱ የራሱ ችግር ነው ማለት ክፉ ነገር አይደለም። ሆን ብሎ የሚበተንበትን መንገድ መተለም ግን ይሁነኝ ብሎ ወደ ጥፋት ማምራት ነው።
ከአንድ ተቋም፣ መ/ቤት የፖለቲካ ፓርቲ፣ ድርጅት ወይም ፓርቲ፣ በማናቸውም መዘዘኛ ግለሰቦችን ወይም ቡድኖችን ለመቀነስ/ለማስወገድ እርምጃ መውሰድ (ዱሮ ሌኒን Purging is purfying ይለው ነበር)/ ማባረር ማጥራት ነው እንደማለት ነው/ በደፈና ሲያዩት ቀላል ይመስላል። በውስጡ ያዘለው ነገር ግን ውስብስብ ነው። ቢያንስ ሶስት ነገሮችን ያዝላል፡-
1ኛ/ በማን ይተኳል 2ኛ/ ልምዱን በምን ያካክሰዋል? 3ኛ/ በእድሜ ብቻ የሚበለጽገው ብስለት ከወዴት ያመጣዋል? ከዚህ በተረፈ ግን ያ የተወገደ ወይም የተባረረ ግለሰብ ቡድን ወዴት ይሄዳል፣ ከማን ይወዳጃል? ድንገት ከባላንጣ ቢወግን ምን አይነት መከላከያ አለ? ወዘተ በታሪክ ሆኖ ዛሬ ተቋሞቻችን፣ ፓርቲዎቻችን መፍትሄ ያላበጁላቸው፣ ዝግጅት የማያደርጉባቸው ክስተቶች ናቸው። የፖለቲካ ሃይል መመናመን፣ መሰነጣጠር፣ ተከፋፍሎም የእኔ ሃይል የሚያክል የታለ ብሎ በባዶ መኩራራት፣ ከእኔ የወጣ ከሀዲ ከእኔ ጋር ያለው ሀቀኛ ቢኖር ፍጹም ማለት ወዘተ ብርቱ ጉድለቶቻችን ተደጋጋሚ ድክመቶችን ናቸው። እነዚህን ሁሉ የሚያካትትልን ደግሞ ወደሌላ የምንልከው ውንጀላ ወደሌላው የምንለኩሰው ጥይት መልሶ ራሳችንን ሊያጠፋን እንደሚችል ማሰባችን ነው። ሁሉም የጊዜ ጉዳይ ነዋ!  ፈረንጆች ወደፊት ተወርውሮ መልሶ ወደራስ መጥቶ የሚወጋ ቀስት/ሹል እንጨት ቡመራንግ ይሉታል (Boomerang):: ከዚህ መዳን አለብን። ቀስቱን ሰትረን ከመቀሰታችን በፊት አላማችንንና ግቡን በውል ማጤን አለብን። የምንፈልገውን በፍትሃዊነት መመዘን አለብን።
በዚህ መንፈስ ዛሬን በጋራ እናስብ፣ እንስራ፣ በዓላችንን እናክብር። መልካም የልደት በዓል፡፡



Wednesday, 03 January 2024 20:37

መላ

መላ

የአለምን ጫጫታ ላፍታ ለማስታገስ
ሆድ ውስጡን ባሰሰ፤
ላገኘ በልቡ የህሊና ጩኸት
ከውጩ የባሰ፤
ልቡን ከሆዱጋ'፥ ላልቻለ ማስማማት
በበደል ተከ'ባ፥ ነፍሱን ለደከማት
.
ኑሮ ትግል ጣጣው፥
ንዋይ እድል እጣው፥
ሁሉም ግራ ሆኖ መሄጃ ላሳጣው፤
.
ጊዜ ነው አቃፊው፥
መጥፎን ከጥሩጋ' አጣምሮ አሳላፊው፤
.
ዝምታው ነው ጌታ፥
የጭንቀት ወራትን ባ'ርምሞ 'ሚረታ፤
.
ተስፋ ነው መድሀኒት፥
የነገን ሁኔታ ዛሬ ላይ 'ሚገምት፤
.
ፍቅር ነው መካሪው፥
ውሸትን ገፍትሮ ለእውነት መስካሪው፤
እምነት ነው አዛኙ፤
ጥፋትን ሳይቆጥር የልብን መዛኙ።
✍️ Sami Anteneh]

ዳሽን ባንክና የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ደንበኞች የአየር ትራንስፖርት አገልግሎት ተጠቅመው ክፍያውን ቆይተው የሚከፍሉበትን ‘ጉዞዎ ይቀድማል ክፍያው ይደርሳል’ የተሰኘ አዲስ የክፍያ አማራጭ አገልግሎት ከትላንት በስቲያ ሐሙስ በጋራ አስተዋውቀዋል፡፡  
የዳሽን ባንክ ዲጂታል ባንኪንግ ዋና መኮንን አቶ ዮሐንስ መኮንን እንደገለጹት፤ ‘ጉዞዎ ይቀድማል ክፍያው ይደርሳል’ የተሰኘው አዲሱ  የክፍያ አማራጭ  በደንበኞች ምርጫ መሰረት በ6 ወር ወይም በ12 ወር የብድር ክፍያ የሚሰጥ ነው፡፡  ደንበኞች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ለመሆን በዳሽን ባንክ የሂሳብ ቁጥር መክፈት እንደሚገባቸውና በተጨማሪም በባንኩ ቢያንስ ለሦስት ወራት አገልግሎት ያገኙ መሆን እንደሚገባቸውም አመልክተዋል፡፡
አዲሱን አገልግሎት ለመጠቀም አንድ ደንበኛ አስፈላጊ ቅድመ-ሁኔታዎችን ካሟላ በኋላ በቅርንጫፉ የተፈቀደለትን የብድር መጠን የሚወስድ ሲሆን፤ የተፈቀደለትን ገንዘብ ለመጠቀም የሚያስችል የአንድ ጊዜ መለያ ቁጥር መልዕክትም በተንቀሳቃሽ ስልኩ የሚደርሰው ይሆናል።
 በመቀጠልም ደንበኛው የተሰጠውን መለያ ቁጥር በአየር መንገዱ የሞባይል መተግበሪያ ላይ በማስገባት ትኬት መቁረጥና የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆን ይችላል።
በሁለቱ ተቋማት ስምምነት በቀረበው በዚህ አገልግሎት ተጠቃሚ ለመሆን የሚፈቀደው የብድር ገንዘብ መጠን እስከ ስድስት መቶ ሺ ብር የሚደርስ ነው። የሚፈቀደው ብድር ወለድ የሚታሰብበት ሲሆን፤ ይህም ደንበኛው በመረጠውና ብድሩን በወሰደበት የጊዜ ገደብ ከብድሩ ጋር አብሮ የሚከፈል መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና የንግድ ሥራ አስፈፃሚ አቶ ለማ ያዴቻ በበኩላቸው፤ “የኢትዮጵያ አየር መንገድ ደንበኛ ተኮር አሰራርን እንደመከተሉ የተለያዩ ዘመናዊና ለመጠቀም ቀላል የሆኑ ቴክኖሎጂዎችን እያስተዋወቀ ይገኛል። የምናበለጽጋቸው ቴክኖሎጂዎች ለደንበኞቻችን ምቹ መሆናቸው እንደተጠበቁ ሆኖ የአገር ውስጥ የፋይናንስ ተቋማት ከሚሰጡት አገልግሎት ጋርም የተጣጣሙ እንዲሆኑ እናደርጋለን። ዛሬም አጋራችን ከሆነው የዳሽን ባንክ ጋር በመተባበር ለደንበኞቻችን ያቀረብነው አዲስ የክፍያ አማራጭ ተግባራዊ እንዲሆን የሞባይል መተግበሪያችን ከአዲሱ የክፍያ አገልግሎት ጋር የተቀናጀ እንዲሆን አድርገናል” ብለዋል።
ደንበኞች የተፈቀደላቸው የብድር መጠን ሲያልቅ ማደስ የሚችሉ ሲሆን፤ በአንዴ የወሰዱትን ብድርም ለተለያዩ በረራዎች ከፍለው መጠቀም እንደሚችሉ ታውቋል፡፡  አገልግሎቱ በተለይም በንግድ ስራ ላይ ለተሰማሩ ጅምላ አስመጪዎችና ለዕረፍት ከቤተሰቦቻቸው ጋር ወደ ውጭ ለሚሄዱ ደንበኞች አመቺ ነው ተብሏል።

 በሃዋሳ ከተማ በምሥራቅ ክፍለ ከተማ በ280 ሚሊዮን ብር ወጪ በ700 ካ.ሜ ቦታ ላይ የተገነባው ባለ 3 ኮከቡ ፌኔት ሆቴል፣ ታህሳስ 13 ቀን 2016 ዓ.ም  የክልሉ የሥራ ሃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ተመርቆ አገልግሎት መስጠት ጀመረ፡፡ የዕለቱ የክብር እንግዳ የሲዳማ ክልል ፕሬዚዳንት አማካሪ አቶ ተሰማ ዲማ በምርቃት ሥነስርዓቱ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ “ሃዋሳ የቱሪዝም ከተማ እንደመሆኗ ሆቴሉ ትልቅ አስተዋፅኦ ያበረክታል” ብለዋል።
አዳዲስና ዘመናዊ አገልግሎቶችን ያካተተው ፌኔት ሆቴል፤ የኮንፍረንስ ቱሪዝሙን መደገፍ የሚችሉ የተለያዩ አገልግሎቶችን የሚሰጡ ክፍሎች ጭምር የያዘ ነው ተብሏል፡፡ለ41 ቋሚና 10 ጊዜያዊ ሰራተኞች የሥራ ዕድል ፈጥሯል የተባለው ሆቴሉ፤ የከተማዋን የቱሪስት እንቅስቃሴና ገቢ ለማሳደግ የላቀ አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ ተነግሯል፡፡
በ1992 ዓ.ም በሃዋሳ ከተማ ጥቂት ሰራተኞችን ይዞ በ50ሺ ብር በጀት በኪራይ ቤት የተጀመረው ሥራ፣ ለረዥም ዓመታት በከተማዋ ተወዳጅ ሆኖ ወደዘለቀው ፌኔት ክትፎ ቤት እንዳደገና  አሁን ደግሞ ባለ 3 ኮኮብ ሆቴል ማዋለድ እንደቻለ በምረቃ ሥነስርዓቱ ላይ ተጠቁሟል፡፡  ፌኔት ሆቴል፤ በቀጣይ  ባለ 4 ኮኮብ ሆቴል ለመገንባት ያቀደ ሲሆን፤ ለክልሉ የመሬት ጥያቄ አቅርቦ ምላሽ እየጠበቀ እንደሚገኝ የሆቴሉ ሥራ አስኪያጅ አቶ ጤናዬ ዋርጌ ተናግረዋል፡፡