Administrator

Administrator

ደሞዛቸው በወር 800 ሪያል ይሆናል
ከሁለት ወራት በኋላ 2800 ኢትዮጵያውያንን በቤት ሠራተኝነት ወደ ሣኡዲ አረቢያ ለመላክ የሚያስችል ዝግጅት መጠናቀቁን በጅዳ የሚገኘው ቆንፅላ ፅ/ቤት አረጋግጦልኛል ሲል ሣኡዲ ጋዜጣ ዘግቧል፡፡
150 ያህል ሰራተኛ በአዲስ አበባ ባለ 5 እና ባለ 10 ብር ካርድ እጥረት የተፈጠረው በከተማዋ የካርድ ተጠቃሚዎች በመበራከታቸው መሆኑን ኢትዮ- ቴሌኮም አስታወቀ፡፡ ለካርዶቹ መጥፋት ከተጠቃሚው መብዛት ባሻገር የስርጭት ችግር መኖሩን ለአዲስ አድማስ የጠቆሙት የኢትዮ-ቴሌኮም የኮርፖሬት ኮሚኒኬሽን ኃላፊ አቶ አብዱራሂም አህመድ፤ አከፋፋዮች እጥረት አለ ሲባል አጋጣሚውን ተጠቅመው ዋጋ ለመጨመር ሰው ሰራሽ እጥረት መፍጠራቸውን ገልፀዋል፡፡
በሳምንት 50 ሚሊዮን  የባለ 5 እና 10 ብር ካርዶች ፍጆታ ላይ ይውሉ እንደነበር የጠቆሙት አቶ አብዱራሂም፤ በአሁን ወቅት ከ100 ሚሊዮን በላይ ካርድ እንደሚቀርብ ሰው ሰራሽ እጥረቱን ማሳያም ነው ብለዋል፡፡
ችግሩን በአፋጣኝ ለማቃለል 140 ሚሊዮን ባለ 5 እና 140 ሚሊዮን ባለ 10 ብር ካርዶች በውጭ ሀገር አሳትሞ ወደ ሀገር ውስጥ በማስገባት ላይ መሆኑን የጠቀሱት አቶ አብዱራሂም፤  ችግሩ ከሰኞ ጀምሮ እንደሚቀረፍም አስታውቀዋል፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም ከ89 ዋና የካርድ አከፋፋዮች፣ 600 ንኡስ አከፋፋዮችና ከ120 ሺህ ቸርቻሪዎች ጋር የገበያ ትስስር በመፍጠር ካርዶቹን ለተጠቃሚዎች እንደሚያደርስ ሃላፊው አስረድተዋል፡፡  
ከሠሞኑ በአዲስ አበባ በርካታ አካባቢዎች ባለ 5 እና ባለ 10 ብር የሞባይል ካርዶችን ለማግኘት አስቸጋሪ እንደነበር ለአዲስ አድማስ አስተያየታቸውን የሠጡ ተጠቃሚዎች አስታውቀዋል፡፡ መልማይና ላኪ ድርጅቶች ከኢትዮጵያ መንግስት የሥራ ፈቃድ አግኝተው ሠራተኞቹን ለመላክ በዝግጅት ላይ ናቸው ተብሏል፡፡ ወኪሎቹ በአሁኑ ወቅት ሰራተኞቹን ወደ ሣኡዲ ለመላክ የሣውዲ መንግስት ይሁንታ ብቻ እየተጠባበቁ መሆኑን ተገልጿል፡፡  
በቤት ሠራተኝነት የሚላኩት ወጣቶች በቤት አያያዝና ተያያዥ ሙያዎች በቂ ስልጠና እንደተሰጣቸውና ስለ ሣኡዲ ባህልና አኗኗርም ግንዛቤ እንዳገኙም ታውቋል፡፡
ወርሃዊ ደሞዛቸውም 800 የሳኡዲ ሪያል መሆኑን የጠቀሰው ዘገባው፤ የመጀመሪያ የስራ ውላቸው ለ3 ወራት የሚቆይ ሆኖ፤ በሂደት ይራዘማል ተብሏል፡፡
በቅርቡ የኢትዮጵያ ሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴርና የሣኡዲ መንግስት የሠራተኛ ጉዳይ ሚኒስቴር በቤት ሠራተኞች ጉዳይ ስምምነት መፈራረማቸው ይታወሳል፡፡
በዚህ ስምምነት ከተካተቱት ጉዳዮች መካከል የሣኡዲ መንግስት ለሠራተኞች ተገቢውን ጥበቃ እንዲያደርግ፣ ሰራተኞች በህጋዊ ኤጀንሲዎች ብቻ መላክ እንዳለባቸው፣ የኢትዮጵያ መንግስት ለሠራተኞች በቂ ስልጠና ሰጥቶና ጤንነታቸው የተሟላና ለስራ ብቁ መሆናቸውን አረጋግጦ እንዲልክ የሚሉት ይገኙባቸዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ ተጨማሪ መረጃ እንዲሰጡን የጠየቅናቸው የሠራተኛ እና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ግርማ ሸለመ፤ በሳኡዲ ጋዜጣ የወጣው መረጃ በሳኡዲ የተገኘ እንጂ ከኢትዮጵያ መንግስት በኩል የቀረበ አለመሆኑን ጠቅሰው ብዙም ስለጉዳዩ መረጃ የለንም ብለዋል፡፡ በስምምነቶች መሠረት እየተከናወኑ ያሉ ዝግጅቶች መኖራቸውንም ኃላፊው አክለው ገልፀዋል፡፡

   የተስፋ ብልጭታዎችና የወደፊት አቅጣጫዎች ክፍል 2

    የአትሌት ጥሩነሽ ዲባባ የስፖርት ማሰልጠኛ ማዕከልን አስመልክቶ በክፍል 1 ያቀረብነው ዘገባ ከ224 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ የሆነባቸውን የስፖርት መሰረተ ልማቶች የግንባታ ሂደቶች በመጠኑ የሚዳስስ ነበር፡፡ በክፍል ሁለት የማሰልጠኛ ማዕከሉን ሳይንሳዊ የስልጠና መንገዶች፤ የአሰልጣኞችን የሙያ እና የብቃት ደረጃ  የሰልጣኞች ምልመላ እና ተያያዥ ሁኔታዎችን  እንመለከታለን፡፡   የማሰልጠኛ ማዕከሉን ፍሬያማነት በማንሳት ከተለያዩ አቅጣጫዎች የምንገመግመው ሲሆን የሰልጣኞችን ተስፋና የአሰልጣኞችን የብቃት ደረጃን ማሻሻል ጥያቄ እናነሳለን፡፡ ይህን ልዩ ዘገባ ለመስራት በጥሩነሽ ዲባባ የስፖርት ማሰልጠኛ ማዕከል የትምህርት፣ የስልጠናና የውድድር ዘርፍ ዲያሬክተር ከሆነው አሰልጣኝ ጎሳ ሞላ ፤ በአጭርና መካከለኛ ርቀት እንዲሁም የአንዳንድ የሜዳ ላይ ስፖርቶች አሰልጣኝ ከሆኑት ንጉሴ አደሬ እና ከከፍታ ዝላይ ሰልጣኝ ማልጎኝ ዊል ጋር ቃለምልልሶች አድርገናል፡፡ ከኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት  ኃይሌ ገብረስላሴ ጋርም ተጨማሪ ውይይት የነበረን ሲሆን በማሰልጠኛ ማዕከሉ ዙርያ የተሰሩ የጥናት ፅሁፎችን መርምረናል፡፡  መልካም ንባብ፡፡
እንደመግቢያ
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ሻለቃ ኃይሌ ገ/ሥላሴ ለስፖርት አድማስ እንደገለፀው በኢትዮጵያ መንግስት በቢሊዮን የሚተመን በጀት ወጥቶባቸው የተገነቡ የስፖርት መሰረተ ልማቶች አድናቆት የሚገባቸው ናቸው፡፡ ለዚህም ዋናው ምክንያት የኢትዮጵያ ወጣቶች ስፖርት አካዳሚ፤ የጥሩነሽ ዲባባ የስፖርት ማሰልጠኛ ማዕከልና ሌሎች ተቋማት የቀድሞ ውጤታማ እና ባለታሪክ አትሌቶች የነበራቸውን ህልምና ፍላጎትን ያሳኩ መሰረተ ልማቶች በመሆናቸው ነው ፡፡
ይሁንና አካዳሚውና የማሰልጠኛ ማዕከሉ የዓለምና የኦሎምፒክ ሻምፒዮን የሚሆኑ ምርጥ ስፖርተኞችን ማፍራት ዋንኛ ዓላማቸው መሆን እንዳለበት የሚያሳስበው ኃይሌ፤ የስፖርት መሰረተ ልማቶቹ ተገንብተው ስራ ከጀመሩ በኋላ በሚከተሉት ራዕይና ዓላማ ዓለም አቀፍ ተፎካካሪነትን  ከግምት ውስጥ ባስገባ የአመራር ደረጃ መንቀሳቀስ እንደሚኖርባቸው፣ በሚሰጧቸው አገልግሎቶች ህዝብን ተጠቃሚ የሚያደርጉበት አሰራር እንዲኖራቸው፤  በአስተዳደራቸው የስፖርቱን ባለድርሻ አካላት በማሳተፍ መስራት እንዳለባቸው ይናገራል፡፡
በርግጥም የወጣቶች ስፖርት አካዳሚ፤ የጥሩነሽ ዲባባ ስፖርት ማሰልጠኛ ማዕከልና ሌሎችም የስፖርት መሰረተ ልማቶች ተቀብለው በሚያሰለጥኗቸው ስፖርተኞች ብቻ በመወሰን ታጥረው መቀመጥ የለባቸውም፡፡ ቢያንስ የመሮጫና የልምምድ ትራኮቻቸው፣ የእግር ኳስና የሌሎች ስፖርቶች ሜዳዎች ተገቢውን የቁጥጥር መርሃ ግብር በመዘርጋት ለሁሉም ክፍት መሆን አለባቸው፡፡
ኃይሌ በአስተያየቱ የስፖርት መሰረተ ልማቶች በሚሰጡት አገልግሎት የገቢ ምንጮችን እንዲፈጥሩ፤  በአስተዳደራቸው ልምድ ያላቸው ታላላቅ ስፖርተኞች እና ባለሙያዎችን እንዲያሳትፉ፤ በባለቤትነት የሚያስተዳድራቸው የስፖርት አካል ብቻ እንዲሆን፤ የነባርና የቀደም አትሌቶች አስተዋፅኦ እንዲጠናከር መደረግ አለበትም ይላል፡፡ በተለይ የገቢ ምንጮችን በመፍጠር ረገድ በሆላንድ፤ በጣሊያን፤ በጀርመንና በእንግሊዝ ያሉ ተመክሮዎችን በመንተራስ ከጅምሩ የተገነቡት የስፖርቱ መሰረተ ልማቶች በዚያ የሚሰራውን መከተል እንደሚኖርባቸው ሲያመለክት ብሄራዊ ቡድኖች ማዕከሉን ሲገለገሉ የሚያንቀሳቅሳቸው ፌደሬሽን ክፍያ እንደሚፈፅም እና ይህ አሰራር በየደረጃው እንደሚሰራበት ጠቁሞ፤ ሌላው የህብረተሰብ ክፍል በተመጣጣኝ ክፍያ የስፖርት መሰረተልማቶቹን አገልግሎት እንዲያገኝባቸው መስራት ተገቢ ነው ብሏል፡፡
የማዕከሉ አሰልጣኞች እና ሳይንሳዊ ስልጠና መንገዶች
በጥሩነሽ ዲባባ የስፖርት ማሰልጠኛ ማዕከል የትምህርት፣ የስልጠናና የውድድር ዘርፍ ዲያሬክተር የሆነው አሰልጣኝ ጎሳ ሞላ ነው፡፡ በማዕከሉ ሁለገብ እንቅስቃሴዎች ያለፉትን 7 አመታት ያገለገለው አሰልጣኝ ጎሳ፤ በስፖርት ሳይንስ በተለይ በአትሌቲክስ ስፖርት በመጀመርያ ከባህርዳር ከዚያም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲዎች ሁለት ዲግሪዎችን ተቀብሏል፡፡
አሰልጣኝ ጎሳ ሞላን ጨምሮ በጥሩነሽ ዲባባ ስፖርት ማሰልጠኛ ማዕከል ላይ  እየሰሩ የሚገኙት 20 አሰልጣኞች ናቸው፡፡ ከመካከላቸው ሶስቱ በስፖርት ሳይንስ ሁለተኛ ዲግሪያቸውን ሰርተዋል፡፡ 17ቱ አሰልጣኞች ደግሞ በስፖርት ሳይንስ የመጀመርያ ዲግሪ ያላቸው ሲሆኑ ከእነሱ መካከል  በማዕከሉ ውስጥ እያገለገሉ ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በመስራት ላይ የሚገኙት አምስቱ ናቸው፡፡ ሃያዎቹ አሰልጣኞች በማዕከሉ ለሚገኙት በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰልጣኞች ውጤታማ እና ተመጣጣኝ ስራ ለማከናወን በቂ ናቸው ለማለት አይቻልም፡፡ ከስልጠናው ባሻገር በፊዝዮሎጂ፤ ስነ ምግብና ስነ ልቦና የሚሰሩ ባለሙያዎች ስብስብ ያካተተ አደረጃጀት ወሳኝ እንደሆነ መታወቅ አለበት ፡፡ የአሰልጣኞቹ ብዛት፤ የሙያ ብቃት፤ የትምህርት ደረጃና ልምድ ዓለም አቀፍ ደረጃ በጠበቀ ሁኔታ በማዋቀር የሚሰራበት አዲስ አቅጣጫ ያስፈልጋል፡፡ ይህንንም የስፖርቱ ባለድርሻ አካላት ከሆኑት ከብሔራዊ ኦሎምፒክ ኮሚቴ፤ ከአትሌቲክስና ከሌሎች የስፖርት ፌዴሬሽኖች ጋር በአጋርነት በመንቀሳቀስ መተግበር የሚቻል ይመስለኛል፡፡
አሰልጣኝ ጎሳ ሞላ ለስፖርት አድማስ እንደገለፀው የማዕከሉ አሰልጣኞች በየጊዜው የሙያ ማሻሻያዎች፤ ስልጠናዎችን በመከታተል ብቃታቸውን የማሳደግ ባህል እያዳበሩ መጥተዋል፡፡ በአትሌቶች ላይ ለሚሰሯቸው ስልጠናዎች ወቅቱን የጠበቁ መረጃዎች በቅርበት የሚወስዱ በመሆናቸው  በተለያዩ ምርምሮች እና ጥናቶች የመሳተፍ ፍላጎትና አቅም እየፈጠሩ ይገኛሉም ብሏል፡፡   በርግጥ በማዕከሉ ከሚሰጡ ስልጠናዎች ጋር በተያያዘ ጥናትና ምርምር የሚደረጉባቸው አሰራሮች መሰረት እየያዙ መምጣታቸው የሚያበረታታ ነው። ሆኖም ግን ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር ተቀናጅተው የሚሰሩበት ፖሊሲ አለመኖሩ ዘላቂ ስኬት የሚመዘገብባቸውን ሁኔታዎች የሚያዳክማቸው ሆኗል፡፡ በተለያዩ ደረጃዎች ከሚሰሩ ብሄራዊ ቡድኖች፤ ከክለብ እና ክልል ቡድኖች፤ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እና ዩኒቨርስቲዎች፤ ከነባር እና ልምድ ካላቸው ትልልቅ አትሌቶች እና አሰልጣኞች፤ ከኦሎምፒክ ኮሚቴ፤ ከፌደሬሽኖች ጋር በአጋርነት በመስራት የማዕከሉን ፍሬያማነት በከፍተኛ ደረጃ ማሳደግ ይቻላል፡፡
ማዕከሉ በሚያከናውናቸው ተግባራት እንደትልቅ ተቋም መንቀሳቀስ ይገባዋል፡፡ ለወጣት ስፖርተኞች የስራ እድል መፍጠር እና ስፖርቶችን ማስፋፋት እንደገዘፈ ውጤት ከመቁጠር መውጣት አለበት፡፡ ሰልጣኞቹ የዓለም እና የኦሎምፒክ ሻምፒዮን ለመሆን የሚበቁ፤ በተለያዩ ስፖርቶች የላቁ ውጤቶችን የሚያስመዘግቡ፤ ሪከርዶችንና የውጤት ክብረወሰኖችን በማሳካት ታሪክ የሚሰሩ መሆን አለባቸው፡፡  የወጣቶች ስፖርት አካዳሚ እና የጥሩነሽ ዲባባ የስፖርት ማሰልጠኛ ማዕከል በስፖርት ዩኒቨርስቲ ደረጃ መንቀሳቀስ ይኖርባቸዋል የሚለው ሻለቃ ኃይሌ ገ/ሥላሴ፤ ተቋማቱ በስፖርቱ ምርምርና ጥናት የሚያደርጉ፤ የአሰልጣኞች አሰልጣኝ የሆኑ ባለሙያዎችን የሚያፈሩ፤ ምርጥ እና ኤሊት አትሌቶችን የሚያፈልቁ፤ ከዓለም እና ከኦሎምፒክ ሻምፒዮኖች ጋር በተለያዩ መዋቅሮች ተቀናጅተው የሚሰሩ መሆን እንዳለባቸው ያሳስባል፡፡ ሁለቱም የስፖርት ተቋማት ዓላማቸው ለዓለም አቀፍ ውድድሮች በአካልና በአዕምሮ ከፍተኛ ብቃት ያላቸው፤ ስነ ምግባራቸውን የጠበቁ ምርጥና ወጣት ስፖርተኞች ማፍራት፤ ለባለሙያዎች የአቅም ግንባታ ስልጠና መስጠት፣ ለስፖርቱ ጥራት አስተዋፅኦ የሚሆኑ የጥናትና የምርምር ስራዎች ማካሄድና ውጤቶችን ማሰራጨት እንዲሁም ለተለያዩ ስፖርቶች የዕውቀት ማዕከል መሆን ነው፡፡
በርግጥ አሰልጣኝ ጎሳ ሞላ  ለስፖርት አድማስ እንደተናገረው በማዕከሉ በሚሰጡ ስልጠናዎች  በሳይንሳዊ አሰራሮች እየተጠናከሩ መምጣታቸው ከላይ የተጠቀሱትን ዓላማዎች ለመተግበር የሚያግዙ አበረታች ጅማሮዎች ናቸው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ የሰልጣኞች ምልመላ በመስፈርት ላይ የተመረኮዘ መሆኑ የማዕከሉን አሰራር ሳይንሳዊ እንደሚያደርገው አሰልጣኝ ጎሳ ሲያስረዳ፤ ‹‹የትኛው አትሌት ለየትኛው ስፖርት መግባት ይችላል››  በሚል አስተሳሰብ እንሰራለን በማለት ነው፡፡ በማዕከሉ በኩል የአትሌቲክስ ሰልጣኞች የሚመለመሉት   በየዓመቱ በየክልሉ ተዘዋውሮ በማፈላለግ በሚከናወኑ ተግባራት ነው። በተለይ ለአትሌቲክስ ከ17 ዓመት በታች እድሜ ያላቸው ታዳጊና ወጣቶች ይፈልጋሉ፡፡ ምልመላውን የሚያከናውኑት የማዕከሉ አሰልጣኞች  በአትሌቲክስ አሰልጣኝነት በመስራት ያላቸውን ልምድ ተጠቅመው በስልጠና እንለውጣቸዋለን ብለው የሚያስቧቸውን አትሌቶች በየክልሉ የሚያፈላልጉበት አሰራር በተሻለ መዋቅር ማደግ ይኖርበታል፡፡ አሰልጣኝ ጎሳ ሞላ የምልመላውን ሂደት ሲገልፅ በዕጩ ሰልጣኞች ምልመላ የሚሰማሩ ባለሙያዎቹ ታዳጊዎችና ወጣቶችን በቅርበት ያላቸውን አቅምና የአካል ብቃት እንደሚገመግሙ፤ ይህን ሂደትም በፎቶ እና በቪድዮ ምስሎች አስደግፈው በሙሉ ሃላፊነት ለማዕከሉ እንደሚያቀርቡም ይገልፃል፡፡ በአሰልጣኞቹ አማካኝነት ከየክልሉ በእጩ ሰልጣኝነት የተመለመሉት  ወደ አካዳሚው ከመግባታቸው በፊት ሌላ ፈተና ይጠብቃቸዋል፡፡  የባለሙያዎች ኮሚቴ ምልመላውን ባከናወኑ አሰልጣኞች የሚቀርቡ መረጃዎችን በጥልቀት ይመረምሯቸዋል፡፡ በመጨረሻም በአዳሪነት ገብተው ተከታታይ ስልጠናዎች ለ4 ዓመታት  ወስደው እንዲመረቁ ይደረጋል፡፡ከዓለም አቀፍ ተመክሮዎች መገንዘብ እንደሚቻለው ምርጥ ፐሮፌሽናል አትሌት በማሰልጠኛ ማዕከል ለማፍራት በትክክለኛው ሳይንሳዊ የስልጠና ሂደት ከ8-12 ዓመት ይወስዳል። በአጠቃላይ አንድ ሰልጣኝ ፕሮፌሽናል አትሌት ለመሆን 10 ዓመታትን መሰልጠንና መማር አለበት። ይህንን በጥሩነሽ ማዕከል ለመተግበር በሚያስብ ፖሊሲ መንቀሳቀስ ተገቢ መሆኑን እዚህ ጋር መጠቆም ግድ ይላል፡፡
በሌላ በኩል  ማዕከሉ ሳይንሳዊ አሰራሮችን እንደሚከተል የሚያመለክት ማስረጃ ስልጠናዎች በእቅድ መመራታቸው ነው አሰልጣኝ ጎሳ ሞላ ማብራሪያውን ይቀጥላል፡፡ እያንዳንዱ ሰልጣኝ ዓመታዊ የእቅድ መርሃ ግብር እንደሚወጣለት፤ ስልጠናን የመቀበል አቅም እና የእድሜ ደረጃን ከግምት ውስጥ እንደሚያስገባ፤ በየእለቱ፤ በየሳምንቱ የሚሰጡት ስልጠናዎች በማማከል የሚነደፉ ናቸው። በተጨማሪም ስልጠናውን በእቅድ ከመምራት ባሻገር ለአትሌቱ ዓመታዊ ግብ በማስቀመጥ መስራታችን ምን ያህል ለሳይንሳዊ አሰራር ትኩረት እንደሰጠን የሚያመለክት ነው የሚለው አሰልጣኝ ጎሳ፤ በተለያዩ የስልጠና ደረጃዎች ለእያንዳንዱ ስፖርተኛ በየስፖርት አይነቱ ዓመታዊ ግብ የሚቀመጥለት ወቅታዊ ብቃቱን በማገናዘብ  እዚህ መድረስ አለበት ተብሎ ነው ብሏል፡፡  በአጠቃላይ በማዕከሉ የስልጠና እቅዶቹ ፤ የልምምድ መርሃ ግብሮች፤ የሚመዘገቡ ውጤቶች እና ተያያዥ አሃዛዊ መረጃዎች በሰነድ እና በዲጂታል ማህደር ከስር በስር የሚከማቹ መሆናቸው ተጠናክሮ መሄድ ያለበት ልምድ ነው ፡፡ የማዕከሉን የስልጠና ሂደት ለመተንተን እና በተለያየ አቅጣጫ ለማስላት የሚያግዝ ሳይንሳዊ አሰራር ነው፡፡
ስልጠናዎች በተለያዩ ወቅቶች መከፋፈላቸውም የሚጠቀስ ሳይንሳዊ የስልጠና ሂደት ሲሆኑ፤ የመደበኛ ዝግጅት ወቅት፤ የቅድመ ውድድር ወቅት እና የውድድር ወቅት በመከተል የሚካሄዱት የስልጠና ሂደቶች ልዩ ውጤት የሚያስገኙ ይሆናሉ፡፡ በሳምንት ከሰኞ እስከ ቅዳሜ ለሁሉም አትሌቶች 10 የልምምድ መርሃ ግብሮች ያሉ ሲሆን፤  በጠዋት እና ከሰዓት ተከፋፍለው ሰልጣኞች የስልጠናውን ጫና ተቋቁመውና በቂ እረፍት አድርገው እንዲሰሩም ይደረጋል፡፡ የአትሌቱን መቶ ፐርሰንት ብቃት በየደረጃ መለካት የሚቻለው በእነዚህ ወቅቶች ጠብቆ መስራት ሲቻል ነው የሚለው አሰልጣኝ ጎሳ፤ በአጠቃላይ ከላይ በተጠቀሱት ሳይንሳዊ የስልጠና ሂደቶች የሚነደፉት የስልጠና መርሃ ግብሮች በተለያዩ ዲፓርትመንቶች ከፀደቁ በኋላ ተግባራዊ እንደሚሆኑ በማመልከት ነው፡፡  ከዓመታዊ እቅድ እና ግብ ባሻገር አሰልጣኙ እና ሰልጣኝ አትሌቱ ተስማምተው እየሰሩ መሆናቸውን ተከታተለው የሚያረጋግጡበት መዋቅርም ተዘርግቷል፡፡ አትሌቱ እዚህ እደርሳለሁ ሲል አሰልጣኙም እዚህ አደርሰዋለሁ በሚል ተስማምተው ይሰራሉ፡፡ በየስልጠናው ክፍል  በእቅድ እና በተቀመጠው ግብ መሰረት እንቅስቃሴ መኖሩን የሚመረምሩ ሃላፊዎች አሉ፡፡ በየወቅቱ የውስጥ ምዘናዎች ይደረጋሉ፡፡ ምዘናዎቹ የአካል ብቃት፤ ወቅታዊ አቋም እና የፉክክር ደረጃ የሚፈተሽባቸው ሲሆን አትሌቱ በየጊዜው ስለሚያሳየው ማሻሻያ ክትትትል ለማድረግ የሚያመች ሌላ ሳይንሳዊ አሰራር ነው፡፡ በማዕከሉ የሚሰጡት ስልጠናዎች በሳይንሳዊ መንገድ መካሄዳቸው ከላይ የተዘረዘሩት ስኬቶች ምስጥር እንደሆኑ የሚያስገነዝበው አሰልጣኝ ጎሳ ሞላ፤ ሰልጣኞች በየእለቱ በሚያልፉባቸው የስልጠና መርሃ ግብሮች ምርጥ ውጤት ለማግኘት ጥረት የሚያደርጉበትን ባህል በማዳበራቸው ወደተለያዩ ውድድሮች ሲገቡ በሪከርድ ስኬት እና በሜዳልያ ውጤት የሚደነቁበትን ታሪክ በተደጋጋሚ የሰሩበትን እድል ፈጥሮታል ብሏል፡፡
በአትሌቲክስ ማሰልጠኛ ማዕከላት የምልመላ ሂደት ያሉትን ዓለም አቀፍ ተመክሮዎች በማጥናት መገንዘብ የሚቻለው የጥሩነሽ ዲባባ የስፖርት ማሰልጠኛ ማዕከል ብዙ ክፍተቶች እንዳሉት ነው። የመጀመሪያው አሳሳቢ ክፍተት ብዙዎቹ ሰልጣኞች ለማዕከሉ የሚመለመሉት በአገር አቀፍ ደረጃ  በሚካሄዱ ውድድሮች ክልብ ወይም ክልል ወክለው ከተሳተፉ በኋላ መሆኑ ነው። በማሰልጠኛ ማዕከል ሳይንሳዊ አካሄድ ሰልጣኞች መመልመል ያለባቸው ምንም አይነት የውድድር ተመክሮ ሳይኖራቸው መሆን ነበረበት፡፡ ከ6-10 በሚሆን እድሜያቸው በየትውልድ ስፍራቸው በሚገኙ የስፖርት ማዘውተሪያዎች ያልፋሉ፡፡ ከዚያም ከ10-14 በሚሆን እድሜያቸው መደበኛ የስፖርት ስልጠናዎችን ከመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸው ጎን ለጎን ያዘወትራሉ። ከእነዚህ ሂደቶች  በኋላ ወደ ማዕከሉ እንዲገቡ መደረግ አለበት።
ሻለቃ ኃይሌ ገ/ሥላሴ የስልጠና ሂደቶች በአካዳሚ፣ በማሰልጠኛ ማዕከል፣ በክለብና በክልል ደረጃ ወጥ የሚሆኑበት መዋቅር ካልተዘረጋ ውጤታማ አንሆንም ይላል፡፡ የላቀ ብቃትንና ውጤት የሚያስመዘግብ ፕሮፌሽናል አትሌት ለማፍራት የሚችለው ከስር ተነስቶ ሁሉንም ባለድርሻ አካላት በሚያሳትፍ ብሄራዊ መመሪያ በመስራት ነው ብሎ፤ በቀድሞ አትሌቶች በአዲስ መልክ ተደራጅቶ የሚንቀሳቀሰው ፌዴሬሽን የነበሩ አሰራሮች እና አመለካከቶች ለመቀየር ቢቸገርም አንዳንድ ስርነቀል ለውጦች ለመፍጠር እየሞከረ እንደሚገኝ ገልጿል፡፡ አትሌቶች የሚያልፉበት የስልጠና ሂደት፤ አሰልጣኞች የሚሰሩባቸው የስልጠና መንገዶች ሁሉ ወጥ አለመሆናቸው ዋናው ፈተና እንደሆነባቸው የሚያስገነዝበው ኃይሌ፣ በዛሬው ትውልድ የአትሌቶች ጥረት እና ትጋት ያነሰ መሆኑን በማስተካከል የአካዳሚና የማሰልጠኛ ተቋማት ሰልጣኞችን የመመልመል ሂደት ከዚያም ለሚሰጡ ስልጠናዎች ስኬት የሚያመች መዋቅር መፍጠር እንደሚገባ ያስገነዝባል፡፡
ለአካዳሚ ወይንም ለማሰልጠኛ ማዕከል የሚሆኑ ሰልጣኞች ተገቢውን የዕድሜ ደረጃና የዕድገት ሂደት ጠብቀው የሚደርሱ መሆን እንዳለባቸው ከዚሁ ጋር በማያያዝ ያስገነዝበው ኃይሌ፤ ከቀበሌ ወደ ዞን ከዚያም በከተማ እና በክልልና በክለብ  ደረጃ በሚዘረጉ መዋቅሮች እና የስልጠና ሂደቶች ስርዓቱን ጠብቀው የሚያልፉ ሰልጣኞችን በመመልመል ውጤታማ ስራ መከናወን ይቻላል ብሎ ይህን ተግባራዊ ለማድረግ ደግሞ በአገር አቀፍ ደረጃ የሚሰራበት ወጥ የአትሌቲክስ መመርያ የመዘጋጀቱን አስፈላጊነት ጠቁሟል፡፡ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን ይህን ታሳቢ በማድረግ ዳጎስ ያለ አገር አቀፍ የአትሌቲክስ መመርያ ሲያዘጋጅ ቆይቶ መጨረሻው ምዕራፍ ላይ እየደረሰ ይገኛል፡፡ መመርያው ከፍተኛ ልምድ ባላቸው የአትሌቲክስ ባለሙያዎች በየክልሉ የተደረጉ ጥናቶችና ቅኝቶች መሰረት አድርጎ የተዘጋጀ ሲሆን አትሌት፤ ክለብ፤ አሰልጣኝ እና ስልጠና ምን መሆን አለበት ለሚለው ጥያቄ ምላሽ የሚሰጥ በስልጠናው የእድሜ ገደብ፤ የእድገት ደረጃ እና የአሰራር ሂደት በዝርዝር የሚቀመጥበት ሰነድ ነው። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን ኃይሌ ገብረስላሴ ይህን የአትሌቲክስ መመርያ አስመልክቶ ለስፖርት አድማስ በሰጠው አስተያየት በሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት በተደጋጋሚ በተደረጉ ውይቶች፤ በቀረቡ ትችቶች እና ግምገማዎች ተጠናክሮ ለህትመት በሚበቃበት የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ የሚገኝ ሲሆን በየአምስት አመቱ እየዳበረ እና እየተሻሻለ የሚሄድ ነው ብሏል፡፡
የማዕከሉ ፍሬያማነት ሲለካ
የጥሩነሽ ዲባባ የስፖርት ማሰልጠኛ ማዕከል ስራ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ጉልህ አስተዋፅኦና መነቃቃት መፍጠሩን በተለያዩ ማስረጃዎች ማመልከት እንደሚቻል ለስፖርት አድማስ በዝርዝር ያስረዳው አሰልጣኝ ጎሳ ሞላ፤ በአጭር እና መካከለኛ ርቀት ሩጫዎች እንዲሁም የሜዳ  ላይ ስፖርቶች በአገር አቀፍ ደረጃ የነበረውን ያነሰ ትኩረት መቀየሩን፤ ብዙም ትኩረት በማይሰጣቸው ስፖርቶች ክለቦች እና የክልል ፌደሬሽኖች ንቁ ተሳትፎ እንዲኖራቸው ማነሳሳቱን ይጠቃቅሳል፡፡ በሜዳ ላይ ስፖርቶች፤ በአጭር እና በመካከለኛ ርቀት ተተኪ እና ውጤታማ አትሌቶች እያፈሩ ስለመሆናቸው የማዕከሉ ሰልጣኞች በክለቦች እና በክልል ፌደሬሽኖች ተፈላጊ እየሆኑ እንደመጡ በመግለፅም የማዕከሉን ፍሬያማነት ሊያመላክት ሞክሯል፡፡
ከወር በፊት በአዲስ አበባ በተካሄደው 46ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በአጭርና መካከለኛ ርቀት፤ በዝላይና በውርወራ ስፖርቶች ከተመዘገቡ 10 ክብረወሰኖች ገሚሱን በማዕከሉ ያለፉ ሰልጣኞች ማስመዝገባቸውንና የሜዳልያ ውጤቶችንም በብዛት ማግኘታቸውን የገለፀው አሰልጣኝ ጎሳ ፤  በታዳጊ እና ወጣት ውድድሮች ላይም የማዕከሉ ሰልጣኞች በተለያዩ ጊዜያት  ስኬታማ ሆነዋልም ይላል፡፡ በሌላ በኩል ሰልጣኞች በማዕከሉ ሆነው ከማዕከሉም ወጥተው አገርን በመወከል በዓለም አቀፍ ውድድሮች ውጤታማ መሆናቸውንም በማስረጃነት አንስቷል። በ2015 እኤአ ላይ ቤጂንግ ባስተናገደችው 15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ በ3ሺ ሜትር መሰናክል የተሳተፉት ጅግሳ ቶሎሳ እና ሃይለማርያም አማረ በማዕከሉ 4 ዓመታትን ሰልጥነው የተመረቁ ናቸው፡፡ በተለይ ሃይለማርያም አማረ በሪዮ 31ኛው ኦሎምፒያ ለመሳተፍ የበቃ መሆኑ ትልቅ ውጤት ነው፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን በማዕከሉ በሁለተኛና ሶስተኛ  አመት ሰልጣኝነት የሚገኙ ስፖርተኞች በየክለቦቹ ተሰራጭተው ጠንካራ ውጤት ማስመዝገባቸው ከዚህ ጋር ተያይዞ የሚነሳ ይሆናል፡፡ በአጠቃላይ ማዕከሉ በኮንደሚኒዬም ቤቶች ከ2002 ዓ.ም መስራት ከጀመረበት ጊዜ እንስቶ እስከ 2009 እኤአ ድረስ 445 አትሌቶች  በማስመረቅ ለተለያዩ ክለቦች እና  ቡድኖች አዘዋውሯል፡፡ 113  አትሌቶች  በተለያዩ የእድሜ ደረጃዎች እና የስፖርት ዓይነቶች ለብሄራዊ ቡድን የተመረጡ ሲሆን 31 ወንድና 26 ሴት አትሌቶች በአህጉራዊ ውድድሮች፤   13 ወንድና 11 ሴት አትሌቶች  ደግሞ በዓለም አቀፍ ውድድሮች ሊሳተፉ በቅተዋል፡፡
በርግጥ የማዕከሉን ፍሬያማነት ከላይ በተዘረዘሩት መረጃዎች ለማመልከት ቢቻልም ግን ሌሎች አሳሳቢ ነገሮች ተጋርጠዋል፡፡ በተለይ ማዕከሉ አሁን ባለበት ደረጃ በተለያዩ የዕድሜ ደረጃ ለሚገኙ ብሔራዊ ቡድኖች ተፎካካሪና ውጤታማ አትሌቶችን በሚጠበቅበት ደረጃ እያቀረበ አይደለም። ወደ ማሰልጠኛ ማዕከሉ ከሚቡት 50 በመቶ ያህሉ በተለያዩ ምክንያቶች ትምህርታቸውን ሳይጨርሱ ይወጣሉ፤ ወደ ክለቦች ሲዛወሩ በማዕከሉ ከነበሩበት የስልጠና ደረጃ ወርደው ይሰራሉ፤ በአገር አቀፍ ውድድሮች ያለወቅታቸው እየገቡ ባክነው ይቀራሉ። የአትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ኃይሌ ገ/ሥላሴ በዚህ ዙርያ አስተያየት ሲሰጥ፣ ማዕከሉ ፍሬያማነቱን ለመለካት ለወጣቶች የስራ እድል መፍጠሩን መጥቀስ እንዳማይኖርበት አመልክቶ የሚጠበቀው ውጤት የዓለምና የኦሎምፒክ ሻምፒዮን ለመሆን የሚበቁ ስፖርተኞችን ማፍራት ነው ይላል፡፡
ምናልባትም የማዕከሉ ሰልጣኞችን በአገር አቀፍ ውድድሮች እያገኙ ያሉት ውጤት የሚያበረታታ ቢሆንም በተሟላ መሰረተ ልማት በሚያሰለጥናቸው ስፖርተኞች  ውጤታማ የሆነበትን እድል ከሌሎች ክለቦች ጋር በማነፃፀር እንደስኬት መቁጠሩ ተገቢ አለመሆኑን ሳያስገነዝብ አላለፈም፡፡ በተያያዘ የማዕከሉ ሰፖርተኞች እንደ ክለብ በአገር አቀፍ ውድድሮች ላይ የሚሳተፉበት ሁኔታ መቀየር እንዳለበት የሚመክሩም አሉ የመንግስት ክለብ ተብሎ መወዳደር ተገቢ አለመሆኑን ለመጠቆም ነው፡፡
በከፍታ ዝላይ ሰልጣኝ የሆነው ማልጎኛ ዊልና ተስፋው
በጥሩነሽ ዲባባ የስፖርት ማሰልጠኛ ማዕከል ባደረግኩት  ጉብኝት ከሰልጣኞች አንፃር ብዙ ያደረግኩት ቅኝት እና ውይይት አልነበረም። የሰልጣኞቹን መመገቢያ፤ መኖርያ እንዲሁም የመማርያ ክፍሎችን ተዘዋውሬ ተመልክቼ ነበር። የማዕከሉ ሰልጣኞች ራሳቸውን የሚያስተዋውቅ ወጥ የስፖርት ትጥቅ (ዩኒፎርም) ቢለብሱ ጥሩ ነው፡፡ የስፖርት መሰረተ ልማቶቹን በመንከባከብ፤ በመፀዳጃ ቤት አካባቢ ያሉ የፍሳሽ ችግሮችን በመቆጣጠር በሚመሩበት ዲስፕሊን አርዓያ መሆን እንዳለባቸው ግን ሳልጠቅስ አላልፍም፡፡
ከሰልጣኞቹ መካከል ግን አንዱን በማነጋገር ምን አይነት ስፖርተኛ ከማዕከሉ እየወጣ መሆኑን ለመገንዘብ ሞክሪያለሁ፡፡ የከፍታ ዝላይ ሰልጣኝ የሆነው ማልጎኝ ዊል ነው፡፡ በመላው ኢትዮጵያ ጨዋታዎች ላይ ጋምቤላ ክልልን ወክሎ  በመሳተፍ  ስፖርተኛነቱን ጀምሮ ዛሬ  በማዕከሉ የ2ኛ ዓመት ተማሪ ሆኖ እየሰራ ይገኛል፡፡   
በማዕከሉ በምከታተለው ስልጠና ከፍተኛ ለውጥ እያሳየሁ እና እያደግኩ ነው በማለት ለስፖርት አድማስ የሚናገረው ማልጎኝ ተስፋው ተመርቆ ከወጣ በኋላ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ውድድሮች የሚሳተፍበትን ደረጃ በማሳካት ክብረወሰን እስከማስመዝገብ ነው፡፡ በ46ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በከፍታ ዝላይ 1.95 ሜትር በማስመዝገብ  የብር ሜዳሊያ ያገኘው ማልጎኝ፤ በከፍታ ዝላይ የኢትዮጵያ ሪከርድ የሆነው 2.07 ሜትር እና በዓለም አቀፍ ውድድር ለመካፈል የሚያበቃው ሚኒማ ደግሞ 2.10 ሜትር መሆኑን ጠቅሶ በማዕከሉ ባሳለፈው የሁለት ዓመት ቆይታ 1.95 ሜትር መዝለሉ ወደ እነዚህ የውጤት ደረጃዎች የሚደርስበትን ሁኔታ የሚጨበጥ እንዳደረገውም ተናግሯል፡፡  ከ4 ዓመታት በኋላ ከማዕከሉ ተመርቆ ሲወጣ አገሩን በዓለም አቀፍ መድረክ መወከል እንደሚችል ምናልባትም በከፍታ ዝላይ የዓለም ክብረወሰንን ለመስበር  እንደሚችል እርግጠኛ እየሆነ መጥቷል፡፡
አሰልጣኝ ንጉሴና ሙያቸውን የማሳደግ ጥያቄያቸው
አሰልጣኝ ንጉሴ አደሬ በማዕከሉ የአጭርና መካከለኛ ርቀት  እንዲሁም የሜዳ ላይ ስፖርቶች አሰልጣኝ ሆነው  እያገለገሉ ናቸው፡፡  በሜዳ ላይ ስፖርቶች  እንዲሁም በአጭርና በመካከለኛ ርቀት ቀድሞ ከነበሩት የተሻሉ ስፖርተኞችን ማዕከሉ በማውጣት  እየተሳካለት መሆኑን ለስፖርት አድማስ የተናገሩት አሰልጣኙ፤ በስራቸው የሚከተሏቸው የስልጠና ሂደቶች  የሙያ ብቃታቸውን  በሚያሳድጉበት አቅጣጫ እየወሰዳቸው መሆኑን ይመሰክራሉ።  ከኮተቤ የመምህራን ማሰልጠኛ በስፖርት ሳይንስ ተመርቀው ከዚያ በአሰልጣኝነት ሙያቸው በማገልገል ከ15 ዓመታት በላይ እንደሆናቸው፤ ከጥሩነሽ ዲባባ የስፖርት ማዕከል በፊት በኦሮሚያ ክልል እና በለገጣፎ የአትሌቲክስ ቡድኖች በሙሉ ሃላፊነት የሰሩበትም ልምድ እንዳላቸው ፤ በ800፣ በ1500 ሜትር በዝላይ እና በውርወራ ያሰለጠኗቸው ስፖርተኞች በአህጉራዊና ዓለም አቀፍ ውድድር በመሳተፍም እንደተሳካላቸው አሰልጣኝ ንጉሤ አደሬ ይናገራሉ፡፡ በተለይ በኦል አፍሪካን ጌምስ እንዲሁም በዓለም ወጣቶች ኦሎምፒክ በቻይና ናይጂንግ 2015 ላይ ዋና አሰልጣኝ ሆነው በመስራት አመርቂ ውጤት አግኝተዋል፡፡
በአትሌቲክስ ስፖርት አሰልጣኝነት የሶስተኛ ደረጃ 3 ሰርተፍኬት አለኝ የሚሉት አሰልጣኝ ንጉሴ ግን በማዕከሉ ቆይታቸው የብቃት ደረጃቸውን በተለያዩ ዓለም አቀፍ ስልጠናዎች የሚያሳድጉበት እድል እንዲፈጥርላቸው ይጠይቃሉ፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተፎካካሪ ሆኖ ለመስራት   ደረጃ 4 የአሰልጣኝነት ማዕረግ ማግኘት ይኖርብኛል በማለት  ለስፖርት አድማስ የተናገሩት አሰልጣኝ ንጉሴ፤  ለዚህ አይነት የአሰልጣኝነት ደረጃ በመብቃት የተሻለ ለመስራት አቅም እንዳላቸው ለማስገንዘብ በማዕከሉ በሚገኝ ቢሯቸው ተገኝተን ስራቸውን እንድንታዘብ አድርገው ነበር።  በርግጥም የአሰልጣኝ ንጉሴ አደሬን ቢሮ ለጎበኘ  በአጭርና በመካከለኛ ርቀት እንዲሁም በሌሎች የሜዳ ላይ ስፖርቶች በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ጉልህ ለውጥ ለማምጣት እየሰሩ እንደሆነና ስኬታማ ለመሆን ፍላጎት እንዳላቸው ለመረዳት አይቸገርም፡፡ የሰልጣኞቻቸውን የልምምድ ፕሮግራሞች፣ የውጤት ታሪክና የመሻሻል ሂደቶች በየዕለቱ እየመዘገቡ በአጀንዳቸው ያሰፍራሉ። በቢሯቸው በተለያዩ ቦታዎች በተቀመጡ ቦርዶችና ግድግዳዎች ላይ የተለያዩ ቻርቶች፣ ግራፎች እና ሌሎች  አሀዛዊ መረጃዎች ለጥፈዋል፡፡ ተገቢውን የሙያ ማሻሻያ  የሚያገኙ ከሆነ ያለጥርጥር በኢትዮጵያ አትሌቲክስ በአጭርና መካከለኛ ርቀት፣ እንዲሁም በሜዳ ላይ ስፖርቶች የላቁ ውጤቶችን እንደሚያስመዘግቡ በልበ ሙሉነት መመስከር ይቻላል፡፡
በተለይ ከስልጠና ስራቸው ጎን ለጎን ከአሰላ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በአትሌቶች አመጋገብ ላይ ልዩ ጥናትና ምርምር እያደረጉ መሆናቸውም የሙያ ማሳደግ ጥያቄያቸውን ተገቢነት የሚያመለክት አብይ ማስረጃ ነው፡፡ አትሌቶች የተጠና የአመጋገብ ስርአት እንዲኖራቸው ለማስቻል ነው፡፡
ይቀጥላል

  የቻይና የጠፈር ተመራማሪዎች በቀጣዩ አመት ወደ ጨረቃ በሚያደርጉት ቼንጅ ፎር የተባለ የጠፈር ምርምር ተልዕኮ፣ በጨረቃ ላይ ድንች ለማብቀል ማቀዳቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ተመራማሪዎቹ ዕጽዋትና ነፍሳት በጠፈር ላይ መራባት የሚችሉበትን ዕድል ለመፍጠር የሚያደርጉት ምርምር አካል ነው በተባለው በዚህ ዕቅድ፤ በምርምሩ የሚገኙ ውጤቶች የሰዎችን በጠፈር ላይ የመኖር ዕድል ለመፍጠር ለሚከናወኑ ስራዎች በግብዓትነት እንደሚያገለግሉ ተነግሯል፡፡
በ2015 ለእይታ በበቃው ዘ ማርቴን የተሰኘ የሳይንስ ፊክሽን ፊልም ላይ ማርስ ውስጥ ብቻውን የቀረን አንድ ገጸባህሪ ወክሎ የሚጫወተው ታዋቂው የፊልም ተዋናይ ማት ዴመን፣ ህይወቱን ለማዳን የድንች ማሳ ሲያዘጋጅ እንደሚታይም ዘገባው አስታውሷል፡፡

  የአገሪቱ መንግስት የቅንጦት መኪና መጠቀም መብታቸው ነው ብሏል

       በሞዛምቢክ የፓርላማ አባላት ለሆኑ የገዢው ፓርቲና የተቃዋሚ ፓርቲ ከፍተኛ ባለስልጣናት በ3.8 ሚሊዮን ዶላር ወጪ 18 ዘመናዊ መርሴድስ ቤንዝ የቅንጦት መኪኖች መገዛታቸው፣ በአገሪቱ ዜጎች ዘንድ ከፍተኛ ቁጣ መቀስቀሱን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መንግስት ለፓርላማ ቋሚ ኮሚቴዎች አመራሮች አገልግሎት ይሰጡ ዘንድ ከፍተኛ ገንዘብ ወጪ አድርጎ ውድ መኪኖችን መግዛቱ፣ በተለይም የማህበራዊ ድረገጽ ተጠቃሚ በሆኑ የአገሪቱ ወጣቶች፣ ከፍተኛ ተቃውሞ እንደገጠመው ዘገባው ገልጧል፡፡
በርካታ የማህበራዊ ድረገጽ ተጠቃሚ ሞዛምቢካውያን፣ “አገሪቱ በከፋ የፋይናንስ እጥረት በተጠቃችበት በዚህ አስቸጋሪ ወቅት ይህን ያህል ገንዘብ አውጥቶ፣ የቅንጦት መኪና መግዛት፣ በዜጎች ላይ መቀለድ ነው” በሚል ድርጊቱን በስፋት አውግዘውታል፡፡ የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች፣ ቡድኖችና የሲቪክ ማህበራት ድርጊቱን በጽኑ ቢቃወሙትም፣ የአገሪቱ ብሄራዊ የበጀት ቢሮ ዳይሬክተር ሮግሪዮ ንኮሞ ግን፣ የፓርላማ ቋሚ ኮሚቴዎች አመራሮች፣ ”የቅንጦት መኪና መጠቀም መብታቸው ነው” ሲሉ ትችቱን ማጣጣላቸውን ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

  ትውልደ ኢትዮጵያዊው አቤል ተስፋዬ 6ኛ ደረጃን ይዟል

     ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፤ የ2017 የአለማችን ከፍተኛ ተከፋይ 100 ዝነኞችን ዝርዝር ሰሞኑን ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ አምና በ22ኛነት ደረጃ ላይ የነበረው ታዋቂው ድምጻዊ ሻን ዲዲ ኮምብስ፣ ባለፉት 12 ወራት፣ የ130 ሚሊዮን ዶላር ገቢ በማግኘት ዘንድሮ የአንደኛነት ደረጃን ይዟል፡፡
ባለፈው አመት በ34ኛ ደረጃ ላይ የነበረቺው ታዋቂዋ ድምጻዊት ቢዮንሴ ኖውልስ፣ ዘንድሮ 105 ሚሊዮን ዶላር በማፍራት  የሁለተኛነት ደረጃን ስትይዝ፣ በአመቱ በድምሩ 95 ሚሊዮን ዶላር ያፈራቺው እንግሊዛዊቷ የ”ሃሪ ፖተር” መጽሃፍት ደራሲ ጄ ኬ ሮውሊንግ በበኩሏ የሶስተኛነቱን ደረጃ ይዛለች፡፡
ካናዳዊው የሂፕ ሆፕ አቀንቃኝ ድሬክ በ94 ሚሊዮን ዶላር፣ የአለማችን የወቅቱ የእግር ኳስ ኮከብ ክርስቲያኖ ሮናልዶ በ93 ሚሊዮን ዶላር አራተኛና አምስተኛ ደረጃን የያዙ ሲሆን፣ በአለም የሙዚቃ መድረክ እጅግ ደምቆ የወጣው ትውልደ ኢትዮጵያዊው ድምጻዊ አቤል ተስፋዬ በበኩሉ፤ በአመቱ 92 ሚሊዮን ዶላር ገቢ በማግኘት የአለማችን ስድስተኛው ከፍተኛ ተከፋይ ሆኗል፡፡
ሙዚቀኞች፣ የፊልም ተዋንያን፣ ስፖርተኞች፣ ደራሲያንና በሌሎች መስኮች አለማቀፍ ዕውቅናን ያተረፉ ዝነኞች  በተካተቱበት በዘንድሮው የፎርብስ መጽሄት የአለማችን ከፍተኛ ተከፋይ 100 ዝነኞች ዝርዝር ውስጥ፣ 16 ሴቶች ብቻ እንደተካተቱ የጠቆመው ፎርብስ፤ ከፍተኛውን ገቢ ያገኘቺው ቢዮንሴ ኖውልስ መሆኗንም አመልክቷል፡፡
በዝርዝሩ ውስጥ የተካተቱት የአመቱ የአለማችን ዝነኞች ባለፉት 12 ወራት ያፈሩት ሃብት በድምሩ ከግብር በፊት 5.15 ቢሊዮን ዶላር እንደሚደርስም ፎርብስ አስታውቋል፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፤ ሳኡዲን በመካከለኛው ምስራቅና በምዕራቡ አለም ሽብር ወንጅለዋል

    የኢራኑ የሃይማኖት መሪ አያቶላህ አሊ ሃሚኒ፤”አሸባሪውን ቡድን አይሲስን የፈጠረቺው አሜሪካ ናት፤ አይሲስንና ሌሎች አሸባሪዎችን እየተዋጋሁ ነው የምትለውም ውሸቷን ነው” ሲሉ መናገራቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
አሜሪካ አይሲስንና አሸባሪዎችን እየተዋጋሁ ነው በማለት የምታሰራጨው መረጃ ከእውነት የራቀ ነው ያሉት አያቶላህ አሊ ካሚኒ፤ በመካከለኛው ምስራቅ አገራት አለመረጋጋት እንዲፈጠር አድርጋለች በማለትም አሜሪካን ወቅሰዋል፡፡
“የአሜሪካ መንግስት ኢራን ራሷን የቻለች አገር ሆና እንዳትቀጥል ይፈልጋል፤ በሁለቱ አገራት መካከል የተከሰቱት አብዛኞቹ ችግሮችም መፍትሄ የማይገኝላቸው ናቸው” ሲሉ ሰሞኑን ከኢራን ከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር ባደረጉት ስብሰባ መናገራቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡
የኢራኑ የሃይማኖት መሪ አያቶላህ አሊ ሃሚኒ፤ አሜሪካና ወዳጇ የሆነቺው ሳኡዲ አረቢያ አይሲስን ጨምሮ በኢራን የሽብር ጥቃት በመፈጸም የሚታወቁ ሌሎች አሸባሪ ቡድኖችን በገንዘብ ይደግፋሉ ሲሉም ወቅሰዋል፡፡  በተያያዘ ዜና ደግሞ፣ የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሞሃመድ ጃቫድ ዛሪፍ፤ ሳኡዲ አረቢያ በመካከለኛው ምስራቅና በምዕራቡ አለም እየተፈጸሙ ለሚገኙ የሽብር ጥቃቶች ድጋፍ ትሰጣለች በሚል መውቀሳቸውን ሮይተርስ ዘግቧል። እ.ኤ.አ በ1979 የተከሰተውን የኢራን እስላማዊ አብዮት ተከትሎ፣ ሁለቱ አገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን ማቋረጣቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ፕሬዚዳንት ትራምፕም ስልጣን ከያዙ ጀምሮ ባሉት ጊዜያት የኦባማ አስተዳደር ከኢራን ጋር የተቋረጠውን ግንኙነት ለማደስ የጀመረውን እንቅስቃሴ እንደሚያቋርጡ በተደጋጋሚ ሲናገሩ መደመጣቸውን ገልጧል፡፡
ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በቅርቡ በእስራኤል ባደረጉት ጉብኝት፣ “ኢራን ሽብርተኞችን በገንዘብና በስልጠና መደገፏን ልታቆም ይገባል” ሲሉ መናገራቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ኤርትራና ጅቡቲ እነ ሳኡዲን መደገፋቸው ሳያስቆጣት አልቀረም ሞሮኮና ኢራን ለኳታር የምግብ እርዳታ ልከዋል

     ኤርትራና ጅቡቲ በመካከለኛው ምስራቅ በተቀሰቀሰውና ከሰሞኑ ተባብሶ አገራትን ለሁለት በከፈለው የኳታር ጉዳይ፣ ከሳኡዲ አረቢያና አጋሮቿ ጎን እንደሚቆሙ ማስታወቃቸውን ተከትሎ፣ ኳታር በሁለቱ አገራት መካከል ግጭት በፈጠረው አካባቢ አስፍራቸው የነበሩ የሰላም አስከባሪ ወታደሮቿን ማስወጣቷ ተዘግቧል፡፡
ኤርትራና ጅቡቲ ከሰሞኑ ባወጡት መግለጫ፤ ኳታርን የሽብርተኝነት አጋር በሚል ካገለሉት የእነ ሳኡዲ አረቢያ ቡድን ጎን እንደሚቆሙ በይፋ ማስታወቃቸው የኳታርን መንግስት ሳያስከፋው እንዳልቀረና አገራቱ በይገባኛል ሲጋጩበት ከነበረው የድንበር አካባቢ የሰላም አስከባሪ ወታደሮቹን ለማስወጣት እንደገፋፋው ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
የኳታር መንግስት የሰላም አስከባሪ ወታደሮቹን ከአካባቢው ማስወጣቱን ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ ቢያስታውቅም፣ ውሳኔውን ለማስተላለፍ የገፋፋውን ምክንያትም ሆነ ያስወጣቸውን ወታደሮቹን ብዛት በተመለከተ ግልጽ መረጃ አለመስጠቱን ዘገባው ገልጧል፡፡
እ.ኤ.አ በ2008 ኤርትራና ጅቡቲ በሚያዋስናቸው ድንበር ላይ በሚገኝ አንድ ስፍራ ላይ የይገባኛል ጥያቄ በማንሳት ግጭት ውስጥ መግባታቸውን ያስታወሰው ሮይተርስ፤ የድንበር ውዝግቡ ወደ ግጭት ማምራቱን ተከትሎ፣ ኳታር የሰላም አስከባሪ ወታደሮቿን በአካባቢው ማስፈሯን ገልጾ፣ አገራቱ በሰሞኑ ውዝግብ ከእነ ሳኡዲ ጎን መቆማቸው ኳታርን ለእዚህ ውሳኔ እንደገፋፋት ጠቁሟል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ ሞሮኮና ኢራን ሽብርተኝነትንና አሸባሪ ቡድኖችን ትደግፋለች በሚል ከተለያዩ አገራት ውግዘት ወደገጠማትንና ከፍተኛ የምግብ እጥረት ወደሚያሰጋት ኳታር የምግብ እርዳታ መላካቸውን አስታውቀዋል፡፡ የሞሮኮ መንግስት ለኳታር የምግብ እህል በአውሮፕላን መላኩን ባለፈው ረቡዕ ያስታወቀ ሲሆን፣ ጉዳዩ ከሰብዓዊ ድጋፍ እንጂ ከፖለቲካ ጋር እንዳይገናኝብኝ ሲል የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ አበክሮ ማስታወቁ ተዘግቧል፡፡ ኢራንም በተመሳሳይ ሁኔታ በአራት የጭነት አውሮፕላኖች የምግብ እህል ወደ ኳታር መላኳን ያስታወቀች ሲሆን፣ በቀጣይም በየዕለቱ 100 ቶን ፍራፍሬና አትክልት ወደ ኳታር ለመላክ ማቀዷን ዘ ኢንዲፔንደንት ጠቁሟል፡፡
የኳታር የፋይናንስ ሚኒስትር ባለፈው ሰኞ በሰጡት መግለጫ፤ የአለማችን እጅግ ሃብታም አገር የሆነቺው ኳታር ከውግዘቱ ጋር ተያይዞ ሊገጥማት የሚችለውን ቀውስ በብቃት መቋቋም የሚያስችላት በቂ ሃብት አላት ሲሉ መናገራቸውን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
 ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ በኳታርና በጎረቤት አገራት መካከል የተፈጠረው ችግር፣ የየአገራቱ ዜጎች የሰብዓዊ መብቶች እንዲጣሱ በር የሚከፍት መሆኑን በመጠቆም፣ ሁሉም አገራት የዜጎችን መብት ላለመጣስ እንዲጥሩ፣ የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽነር፣ ዛኢድ ራድ አል ሁሴን ባለፈው ረቡዕ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
የተባበሩት አረብ ኤሚሬትስና ባህሬን፤ ለኳታር ያላቸውን ሃዘኔታ ገልጸዋል ባሏቸው ሰዎች ላይ “የእስርና የገንዘብ ቅጣት እንጥላለን” የሚል ዛቻ እየሰነዘሩ ነው ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ይህም የሰብዓዊ መብት ጥሰት በመሆኑ አገራቱ ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

  ጊዜው ያለፈበት ክሎሪንና ፍሌቨር ለጁስ ምርት ይውላል 20 ዓመት ያለፋቸው የሳሙና ኬሚካሎች ተገኝተዋል
    ምርቶቹ የሚሸጡት ከመዲናዋ በራቁ አካባቢዎች ነው ሠራተኛን መስደብ፣ ማዋረድና ማሸማቀቅ የተለመደ ነው
           ከጋዜጣው ሪፖርተር

       በሰበታ ከተማ የሚገኘው ፓስፊክ ኢንዱስትሪ ኃ.የተ.የግል ማህበር፤ አቶ መፍቱህ አብዱልጋፋር በተባሉ ባለሀብት ባለቤትነት የሚመራ ፋብሪካ ነው። ፓስፊክ ኢንዱስትሪ፤ ሦስት የተለያዩ ምርቶችን እያመረተ ለገበያ ያቀርባል - ‹‹ማሩቲ፣ ዊኒስታርና ክላሲክ›› የተባለ የልብስ ሳሙና፣ ‹‹ፕሮሚስ›› የተባለ የታሸገ ውሃ እና “ማርች ኦሬንጅና ማርች ማንጎ” የተባሉ ጁሶች ናቸው። ምርቶቹ በሙሉ የሚሸጡት ግን ከአዲስ አበባ በራቁ ክልሎች መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡  
ከድርጅቱ በቅርቡ የተባረሩ ሠራተኞች ለአዲስ አድማስ በዝርዝር እንደገለጹት፤ ”ሦስቱም ምርቶች የሚሠሩት ጊዜያቸው ባለፈ (ኤክስፓየር ባደረገ) ጥሬ ዕቃ ነው፡፡ ስለዚህ በአዲስ አበባና አካባቢው ለገበያ አይቀርቡም፤ ራቅ ወዳሉ የክፍለ ሀገር ከተሞች ተወስደው ነው የሚሸጡት”
ሠራተኞች አይበረክትለትም እየተባለ በሚነገርለት ፓስፊክ ኢንዱስትሪ፤ ጊዜያቸው ያለፈባቸው ኬሚካሎችና ሌሎች ጥሬ ዕቃዎች ለምርት እንደሚውሉ በቅርቡ ከድርጅቱ የለቀቁና የተባረሩ ሰራተኞች አጋልጠዋል፡፡ በአንድ ጊዜ ስቶር ሱፐር ቫይዘርም፣ ካሸርም፣ ፐርሶኔልም፣ ነዳጅ ቀጂም ሆና ትሰራ እንደነበር የገለጸችው የቀድሞ ሠራተኛ፤ በተቀጠረች በአንድ ወር ከ15 ቀኗ መባረሯን ትናገራለች፡፡ በዚህች አጭር ቆይታዋ ግን ጊዜያቸው ያለፈባቸው ጥሬ እቃዎች በፋብሪካው ውስጥ መኖራቸውን ብቻ ሳይሆን ለጁስና ለታሸገ ውሃ ምርት ጥቅም ላይ ይውሉ እንደነበር ማረጋገጧን ጠቁማለች፡፡  
“እዚህ ግቢ ውስጥ የመጠቀሚያ ጊዜው ያለፈ (ኤክስፓየር ያደረገ) ክሎሪን አለ፡፡ መጋዘኑን የምናውቀው ሁለት ሰው ብቻ ነን፣ እኔና የሚደባልቀው (ሚክስ የሚያደርገው) ልጅ ብቻ። ለረዥም ጊዜ በመቆየቱ ጊዜው ያለፈበትን ይህን ክሎሪን፤ ለውሃም ለጁሱም ምርት ይጠቀሙበታል። አንድ ቀን ወደ ክሎሪኑ ጠጋ ስል ሽታው አልተመቸኝም፡፡ ልጁን፤ እስቲ ይህን ክሎሪን አውጣልኝና የመጠቀሚያ ጊዜውን ልየው አልኩት፤ አወጣልኝና አየሁት፡፡ በ2012 ኤክስፓየር ያደርጋል- ይላል፤ አሁን 2017 ነው፤ ኤክስፓየር ካደረገ 5 ዓመት አልፎታል ማለት ነው፡፡”
በዚሁ የመጠቀሚያ ጊዜው ባለፈበት ክሎሪን የተነሳም ከባለቤቱ ጋር ፍጥጫ ውስጥ እንደገባችና እውነቱን ፊት ለፊት እንደነገረቻቸው ይህችው የቀድሞ ሰራተኛ ለአዲስ አድማስ አስረድታለች - የተለወጠ ነገር ባይኖርም፡፡
“የፋብሪካው ሰራተኞች ውሃ ከሚመረትበት ክፍል መጥተው፤ ክሎሪን ስጪን አሉኝ፤ አልሰጥም አልኳቸው፡፡ ለባለቤቱ ነገሩት፤ ስልክ ደውሎ ጮኸብኝ፡፡ ‹‹ያለመስጠት የእኔ ኃላፊነት ነው፤ መጥተህ አነጋግረኝ›› አልኩት፤ መጣ ‹‹ይህን ውሃ‘ኮ የሚጠቀሙት ሕፃናት ሊሆኑ ይችላሉ፤ ምናልባትም ያንተም ልጆች ሊጠቀሙበት ይችሉ ይሆናል፤ ከ5 ዓመት በፊት ኤክስፓየር ያደረገ ክሎሪን እንዴት ትጠቀማለህ?!” አልኩት፤ ‹‹በቃ ነገ ወደ ታች ግቢ ይጫናል›› ብሎኝ ሄደ፡፡ ከዚያ በኋላ አንድ ወር ቆይቼ ነው የወጣሁት፤ እስከዚያ ጊዜ ድረስ  ታች  ወደተባለው ግቢ አልተጫነም፤ አሁንም እየተጠቀሙበት ሊሆን ይችላል” ስትል ጥርጣሬዋንና ግምቷን ተንፍሳለች፡፡
“የዛገ ዕቃ፤ ለምግብ ቀርቶ ለመለዋወጫ መጠቀም ክልክል ነው፤ በዚህ ድርጅት ውስጥ የሚጠቀሙት መለዋወጫ በሙሉ የዛገ ነው፡፡” ያለችው የድርጅቱ የቀድሞ ሰራተኛ፤ በጁስ ምርት ውስጥ የሚጨመረው ፍሌቨርም ጊዜው ያለፈበት መሆኑን እንዴት እንደደረሰችበት ለአዲስ አድማስ ጠቁማለች፡፡
“ፍሌቨሩ ከየት አገር እንደሚመጣ በፍፁም አናውቅም፤ ፍሌቨሩን ሌሊት መጥቶ የሚጨምረው ራሱ ነው፤ ቀምማችሁ ጠብቁኝ የሚል ትዕዛዝ ይሰጣል፤ ተቀምሞ፣ ስኳር ተደርጎበት ይጠብቀዋል፤ ሌሊት መጥቶ ፍሌቨሩን ጨምሮ፣ ያመጣበትን መያዣ ዕቃ ይዞ ይሄዳል። ይህን የጁስ አሠራር ማንም ሠራተኛ እንዳያይ የተደረገበት ምሥጢር ምንድን ነው? አንድ ቀን በአጋጣሚ ፍሌቨሩ የመጣበትን ዕቃ አግኝቼ ሳይ፣ ፍሌቨሩ ራሱ ኤክስፓየር ያደረገ መሆኑን ተረዳሁ”  
የመጠቀሚያ ጊዜው ያለፈበትን ክሎሪን ባጋለጠችበት ጊዜ፤ ም/ሥራ አስኪያጁ አቶ ሸረፋ ከማል ‹‹ይሄ አንቺን አይመለከትሽም፤ ከእሱ ጋር መጋፈጥ ማለት ከግድግዳ ጋር መጋጨት ነው›› ሲል ሊያስፈራራት እንደሞከረ አስታውሳ፤ እሷም በበኩሏ፤ ‹ይቅርታ አድርግልኝ! እኔ ፈሪ ትውልድ አይደለሁም›› በማለት እንደመለሰች ተናግራለች፡፡
ድርጅቱ በአጠቃላይ ከባድ ችግሮች አሉበት ያለችው ደግሞ የ”ፕሮሚስ ውሃ” የፋይናንስ ሰራተኛ በመሆን ለ10 ወራት ገደማ ከሰራች በኋላ፣ ባለቤቱና ም/ሥራ አስኪያጁ ከባድ ዕዳ ፈጥረው፣ በዋስትና ያስያዘችውን የአሮጊት እናቷን መኖርያ ቤት እንዳያሸጧት ፈርታ፣ ሥራዋን በገዛ ፍቃዷ የለቀቀችው የድርጅቱ የቀድሞ ሠራተኛ ናት፡፡ ድርጅቱ ለጁስና የታሸገ ውሃ ምርት የሚጠቀምባቸውን ጊዜ ያለፈባቸው ጥሬ ዕቃዎች በዝርዝር ታውቃለች፡፡ እንደውም በቆጠራ ወቅት የአገልግሎት ጊዜ ያለፈባቸው ፍሌቨሮችና ስታርቾች አግኝተው፣ ለአስተዳደሩ ሪፖርት ማድረጋቸውን ጠቁማለች፡፡   
“እኔ በዚያ ድርጅት የሠራሁት 10 ወር ያህል ነው፡፡ በመጨረሻ ልወጣ አካባቢ ንብረት ቆጠራ ገብቼ ነበር፡፡ እንዳየሁት ከሆነ፣ የሚመረተው ውሃም ሆነ ጁስ በትክክል ችግር አለበት፡፡ የንብረት ቆጠራውን ያደረግነው እኔና የአስተዳደር ሠራተኛው ነበርን፡፡ ለምሳሌ፣ የሳሙና ኬሚካል የሚቀመጥበት ክፍል ውስጥ 20 ዓመት ያለፋቸው ኬሚካሎች፣ ኤክስፓየር ያደረጉ 40 ጀሪካን የጁስ ፍሌቨርና ስታርቶች አግኝተናል፡፡ እኔና የአስተዳደር ሰራተኛው፤ ጊዜያቸው ያለፈባቸው ጥሬ ዕቃዎች በሙሉ መወገድ አለባቸው ብለን የጻፍነው ደብዳቤ በእጄ ይገኛል”
አዲስ አበባ አፍንጫ ስር በሰበታ ከተማ እንዲህ ያለ የህብረተሰቡን ጤና የሚጎዳ፣  የተቀነባበረ ሕገ-ወጥ ተግባር ሲፈፀም፣ ጉዳዩ የሚመለከታቸው የመንግስት ተቆጣጣሪ አካላት እንዴት ሳይደርሱበት ቀሩ? ማሰኘቱ አይቀርም፡፡ ሠራተኞች እንደሚናገሩት፤ የመንግስት ተቆጣጣሪ አካላት በየጊዜው ይመጣሉ ግን እንዴት እንደሆነ አይታወቅም፤ ሰውየው ‹‹ውሃ አድርጎ” አሳምኖ ይመልሳቸዋል፡፡
በካሸርነትና በስቶር ሱፐርቫይዘርነት የሰራችው የቀድሞ የድርጅቱ ተቀጣሪ፤ ‹‹እሱ እጁ ረዥም ነው፤ በትክክለኛ መንገድ 300 ሺህ ብር ከሚከፍል በሕገ-ወጥ መንገድ 3 ሚሊዮን ብር ቢያወጣ ይቀለዋል›› ብላለች፡፡
በፋብሪካ የሚመረት የምግብ ሸቀጥ ከፍተኛ ጥንቃቄ ያስፈልገዋል፤ ነገር ግን ድርጅቱ ከእንደዚህ ዓይነቱ ሥልጣኔም ሆነ የሠራተኞች ደህንነት አጠባበቅ ጉዳዮች ጋር አይተዋወቅም ብላለች- የቀድሞ የድርጅቱ ሠራተኛ፡፡
“በዚህ ፋብሪካ የሚሠሩ ልጆች ጓንት አይጠቀሙም፤ አይሰጣቸውማ! በክሎሪንና በሶዳ ዕቃ ያጥባሉ፤ በዚያው እጃቸው ጁስ ምርት ውስጥ ይገባሉ፡፡ ክሎሪንና ሶዳው ወደፊት፣ በእጃቸው ላይ በሽታ ሊያስከትልባቸው ይችላል፡፡ የመቶ ብር ጓንት ገዝቶ ቢሰጣቸው ምን ችግር አለበት? የሚገርምህ ነገር እኔ ነኝ በመቶ ብር ጓንት ገዝቼ የሰጠኋቸው። ይህንን ያደረኩበት ምክንያት እህቶቼ ናቸው ብዬ ነው፤ ችግር ነው እዚያ ቦታ የጣላቸው”
“ላቦራቶሪውም ራሱ ብዙ ችግሮች አሉበት” ትላለች - ይህቺው ሠራተኛ፡፡ እዚያ የሚሠሩ ሠራተኞችም ችግሩን እንደሚያውቁት ትናገራለች።
“ነገር ግን እየፈሩ አይናገሩም፡፡ አንዳንዶቹ የቤተሰብ አስተዳዳሪዎች ናቸው፤ ሌሎች ደግሞ የዕለት ጉርስ ማግኛቸው ስለሆነ ‹‹ነገ ብባረርስ?›› በማለት ስህተቱን ለመናገር ይፈራሉ፡፡ ይህን ሕገ-ወጥ አሠራር፣ የሠራተኞችን ጭቆናና ግፍ፤ መንግሥት በጥንቃቄ ቢከታተለው በጣም ደስ ይለኛል፡፡” ስትል አስተያየቷን ሰንዝራለች፡፡
“እውነቴን ነው የምለው እዚያ ግቢ ስገባ ኢትዮጵያ ውስጥ ሳይሆን አረብ አገር ወይም ሌላ የባርነት ሥርዓት የተንሰራፋበት አገር ያለሁ ነው የሚመስለኝ፡፡ ሽንት ቤት እንድትሄድ አይፈቀድልህም፣ ስልክ ተደውሎልህ ማንሳት አትችልም፡፡ ጧት ገብተህ እንደተዘጋብህ ትውላለህ። ሁለተኛው ጓንታናሞ ያለው ፓሲፊክ ኢንዱስትሪ ግቢ ነው፡፡ አንድ ጸሐፊ አለች፤ የኩላሊት በሽተኛ ስለሆነች ሐኪሟ ብዙ ውሃ ጠጪ ብሏታል፡፡ ብዙ ውሃ ስለምትጠጣና ሽንቷ ቶሎ ቶሎ ስለሚመጣባት ሽንት ቤት ትመላለሳለች። ‹‹አንቺ ለሽንትሽ ጊዜ የለሽም እንዴ?›› ተብላለች። ይህን ያህል ሰብአዊ መብት የሚጣስበትና ሕግ የሌለበት ድርጅት ነው።” ብላለች - ሠራተኛዋ፡፡
ስድስት ወር ያገለገለው የድርጅቱ ሰራተኛ የተባረረበት ምክንያት ይገርማል፡፡ ‹‹የድርጅቱ ባለቤት፣ ሥራ አስኪያጅ፣ አስተዳደር… ሁሉም ነገር ባለቤቱ ራሱ ነው›› ይላል - ሠራተኛው፡፡
‹‹ድርጅቱ ከፍተኛ ግብር ከፋይ ነው፡፡ በሥራዬ አጋጣሚ 224 ሺህ ብር ዕዳ አለባችሁ›› የሚል ደብዳቤ  ደረሰኝና ያንን ደብዳቤ ለባለቤቱ ሰጠሁ። ባለቤቱም “አንተን እዚህ ውስጥ ምን አገባህ? ለምንድነው ያመጣኻው?” በማለት ፀብ ተፈጠረ፡፡ የሰራሁበትን ደሞዝና አበል ሳይከፍለኝ ውጣ ብሎ ሰድቦ አባረረኝ›› ብሏል፡፡
ይኸው ሠራተኛ፤ ሌሎች ውሃ አምራች ድርጅቶች በቲቪ፣ በሬዲዮና በጋዜጣ ሲያስተዋውቁ አይቶ ‹‹እኛስ ፕሮሚስን ለምን አናስተዋውቅም?›› የሚል ሃሳብ ያቀርባል፡፡ ባለቤቱ ‹‹ዝም ብለህ ተቀመጥ፤ ይኼ አይሠራም፤ የማያገባህ ነገር ውስጥ አትግባ›› በማለት እንዳሸማቀቁት ተናግሯል፡፡  
የድርጅቱ ሌላው ችግር፣ ሠራተኛ ሲቀጥር ውል አይዋዋልም፡፡ ይሄ ደግሞ ሠራተኞች መብታቸውን እንዳይጠይቁ፣ የሰብአዊ መብት ረገጣ እንዲደርስባቸው እንዳደረጋቸው ተናግረዋል - የድርጅቱ ሠራተኞች፡፡ በሆነው ባልሆነው የሰራተኛውን ክብር አዋርዶ ከሥራ ማባረር፣ ደሞዝ መቆራረጥና ከእነአካቴው መከልከልም ለፓስፊክ ኢንዱስትሪ በጣም የተለመደ ተግባር መሆኑን ሠራተኞች ጠቁመዋል፡፡   
“ውል ስንጠይቅ፤ እኛ ሥራችሁ ላይ ገደብ (ሊሚት) እንዲኖርባችሁ አንፈልግም፤ ይላሉ። ነገር ግን እነሱ በፈለጉት ጊዜ ተነስተው፤ ‹‹ሥራህን ልቀቅ፣ ተባረሃል›› እያሉ ለአንዳንዶች ደብዳቤ ይሰጣሉ፡፡ ብዙዎች ግን ‹‹ዓይንህን እንዳላየው፤ ከነገ ጀምሮ እዚህ ግቢ እንዳትመጣ፤ ምንም መሥራት አትችልም አቅም የለህም፣…›› በማለት ባለቤቱ ሠራተኛውን አዋርዶ ያባርራል። አንድ ሠራተኛ 30 ቀን ሰርቶ ደሞዝ ሲወጣ ቀርቶ፣ በሁለተኛው ቀን ቢመጣ፣ ወር ሙሉ የሠራበት ደሞዙ አይከፈለውም፡፡ ‹‹ደሞዛቸው እንዳይከፈል››፣ “የዚህ ቀን ደሞዛቸው ይቆረጥ” የሚል የመከልከያ ደብዳቤ ለፋይናንስ ይጻፋል፤ በዚህ ዓይነት ደሞዛቸው ሳይከፈል ተመላሽ የሆነባቸው ብዙ ሠራተኞች አሉ”
የክፍለ ሀገር የሳሙና ሽያጭ ሠራተኛው ደግሞ 8 ወር ሰርቶ መባረሩን ተናግሯል፡፡ ‹‹ሰራተኛ ሲባረር ቀርቶ ሲቀጠርም ደብዳቤ አይሰጠውም። ‹አንተ ሌባ ነህ፤ ግቢዬን ለቀህ ውጣልኝ› ነው የሚባለው። የዚህ ዓይነት ስድብና አባባል በተደጋጋሚ ስሰማ ቆይቼ በመጨረሻም በእኔ ላይ ደረሰ፤ ሠራተኛ በግፍ የሚባረርበት መ/ቤት ፓሲፊክ ኢንዱስት ነው›› ብሏል፡፡
“አንድ ሰራተኛ በድርጅቱ ቆየ ቢባል 3 ወር ነው። እኔ 8 ወር ሰርቼ ነው የወጣሁት፤ የሚያውቁኝ ጓደኞቼ ይህን ያህል መቆየቴን ሲሰሙ ይገረማሉ። የባለቤቱ ሰላይ (ጆሮ ጠቢ ነህ) የሚሉኝም አሉ። እኔ የምሸጠው ሳሙና ማሩቲ ክላሲክ ይባላል። ሳሙናው ገበያ ላይ ካሉትና በትልቅነቱ ምርጥ ከሚባሉት አንዱ ነው። ዋጋውም በጣም ርካሽ ነው፡፡ ስለዚህ ገበያውም ውስጥ ገብቷል፡፡ የሚሸጠው ደግሞ ከአዲስ አበባ  ርቀው በሚገኙት  እንደ ሻሸመኔ፣ ዲላ፣ ይርጋጨፌ፣ ጂማ፣ አጋሮ፣ ጌራ፣… በተባሉ ራቅ ራቅ ባሉ የገክልል ከተሞች ነው፡፡ ነጋዴዎቹን ‹‹ይህ ሳሙና ተወዳጅ የሆነው ለምንድነው?›› በማለት ጠይቄአቸው ነበር፡፡ የሰጡኝ መልስ፤ የኅብረተሰቡ የኢኮኖሚ አቅም ዝቅተኛ ስለሆነ ዋጋው ረከስ ያለ ምርት ስለሚመርጡ ነው እንጂ የጥራት ደረጃው ዝቅተኛ እንደሆነ እናውቃለን፤ ብለውኛል፡፡ እኔም አገልግሎት ጊዜው ባለፈ ጥሬ ዕቃ ስለሚሰራ ጥራቱን የጠበቀ እንዳልሆነ አውቃለሁ፡፡” ብሏል የቀድሞው የሽያጭ ሠራተኛ፡፡
የፓሲፊክ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ አቶ መፍቱህ አብዱልጋፋር በበኩላቸው፤ ድርጅቱ የአገልግሎት ጊዜው ባለፈበት ጥሬ ዕቃ ይጠቀማል የሚለውን የሠራተኞች ውንጀላ መሰረተ ቢስ ነው ሲሉ አስተባብለዋል፡፡ ‹‹ይኼ‘ኮ የሀገር ሀብት ነው፤ ለ30 ዓመት የሰራ ፋብሪካ እንዴት እንዲህ ያደርጋል? በፍፁም ከእውነት የራቀ ነው››
የድርጅቱ ሠራተኞች ተፈፅሞብናል የሚሉትን በደል በተመለከተም ተጠይቀው ሲመልሱ፤ ‹‹ሰራተኛው ላይም ምንም በደል አይፈጸምም፤ ሰራተኛ ሲያጠፋ ከመቶ አንድ ሊኖር ይችላል እንጂ በማንም ላብ ላይ በደል አይፈጸምም፡፡ ደሞዙን ከአንድ ዳቦ ወደ ሁለት ዳቦ ለማሳደግ ከመጣር በስተቀር በሰራተኛው ላይ የሚደረግ ጭቆና የለም›› ብለዋል፡፡  

 ከአንድ አመት በፊት በቀዳማዊት እመቤት ሮማን ተስፋዬ፤ የመሰረት ድንጋይ የተቀመጠለትና በቅርቡ ግንባታው የተጠናቀቀው ‹‹ግሪን ላይት አውቶሜካኒክ” የስልጠና ማዕከል ረቡዕ ረፋድ ላይ በይፋ ተመረቀ፡፡ በኪያ ሞተርስና በኮሪያን ኢንተርናሽናል ኮኦፕሬቲቭ ኤጀንሲ (KOICA) ወጪው ተሸፍኖ፣ በወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ የተገነባው ይሄው ማዕከል፤ ባለ 4 ወለል ህንፃ ሲሆን ኢትዮጵያዊያንን ወጣቶች በአውቶሜካኒክ ስልጠና ወስደው ባለሙያ የሚሆኑበት ነው ተብሏል፡፡
ህንፃው ለአውቶ ሜካኔክና ለእጅ ስራ ሙያ ስልጠና የሚያስፈልጉ ቁሳቁሶችን ያሟላ ሲሆን በቀጣይም በተጨማሪ ቁሳቁሶች ተደራጅቶ በአጠቃላይ ለ615 ወጣት ወንዶችና ሴቶች ስልጠና ይዘጋጃል ተብሏል፡፡ በቀጣዩ ግንቦት ስልጠና መስጠት ይጀምራል የተባለው ማዕከሉ፤ የህንፃውን ግንባታ ጨምሮ ለአምስት ዓመት የሚቆይ ፕሮጀክት ሲሆን 220 ወጣቶችን በአውቶ ሜካኒክ፣ 395ቱን ደግሞ በእጅ ስራ ሙያ አሰልጥኖ፣ ራሳቸውን እንዲችሉ የማድረግ እቅድ ይዟል፡፡ ማዕከሉ የራሱ የአስተዳደር ቁመናና ስርዓተ ትምህርት እየተቀረፀለት እንደሆነም ተገልጿል፡፡
ስድስት የመማሪያ ክፍሎች፣ ሶስት ወርክሾፖች፣ አምስት ቢሮዎች፣ አምስት የእቃ ማከማቻ ክፍሎች፣ ሁለት የመምህራን ቢሮዎች፣ አንድ የICT ክፍል፣ አንድ ቤተ መፅሀፍት፣ አንድ ጋራዥና አንድ ላውንጅ አሟልቶ የያዘም ነው ተብሏል ህንፃው፡፡ በዚህ ማዕከል በአውቶ ሞቲቭ ኢንጂን በሌቭል 1 እና በሌቭል 2 በፓወር ትሬይንም እንዲሁ በሌቭል 1እና ሁለት ስልጠና የሚሰጠው ማዕከሉ በቀጣዩ ግንቦት በሁለት ዙር ስልጠና ለመስጠት ሰልጣኞችን መመዝገቡን አስታውቋል፡፡
በምርቃት ስነ ስርዓቱ ላይ የተገኙት የወርልድ ቪዥን ካንትሪ ዳይሬክተር ኤድዋርድ ብራውን ባደረጉት ንግግር፤ “ካንትሪ ዳይሬክተር ሆኜ ከተሾምኩ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የጎበኘሁት ትልቅ ፕሮጀክት በመሆኑ ለእኔ ትልቅ በዓል ነው” ብለዋል። ሌላው በምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ በእንግድነት የተገኙት የአዲስ አበባ ቴክኒክ፣ ሙያና ትምህርት ስልጠና ኤጀንሲ ዳይሬክተር አቶ ዘሩ ስሙር፤ ኮሪያና ኢትዮጵያ ባላቸው ታሪካዊ ግንኙነት በእጅጉ ኢትዮጵያን እየደገፉ መሆኑን ጠቁመው መንግስት በቴክኒክና ስልጠና በርካቶችን ተጠቃሚ እያደረገ ቢሆንም ሁሉንም ስለማያዳርስ እንዲህ አይነት ድርጅቶች የሚያደርጉት ድጋፍ ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡ የኮሪያ አምባሳደር በኢትዮጵያ ሚስተር ሙን ሁዋን ኪም ኢትዮጵያ ለኮሪያ ባለውለታ በመሆኗ ይህን ውለታ ለመመለስ ብዙ ምክንያቶችን እንፈልጋለን፤ ይሄም ፕሮጀክት ውለታ ለመመለስ አንዱ መንገድ ነው ብለዋል፡፡ ማዕከሉ ለሚያከናውነው የ5 ዓመት ፕሮጀክት፤ የ2.5 ሚ ዶላር (57.8) በጀት ተይዞለታል ተብሏል፡፡

 አዲስ አልበሙን አስተዋወቀ

     በኢትዮጵያ ሙዚቃ ወርቃማ ዘመን ለ25 ዓመታት በልዩ ብቃት ዘመን ተሻጋሪ የሙዚቃ ስራዎችን ለአድማጮች ያቀረበው ከያኒ ግርማ በየነ ባለፈው ማክሰኞ በብሔራዊ ቴአትር ከ ‹‹አካሌ ውቤ›› ባንድ ጋር ያቀረበው ኮንሰርት አስደሳችና አዝናኝ እንደነበር ታዳሚያን ገለፁ፡፡ ድምፃዊ፣ የሙዚቃ ቀማሪና አቀናባሪ እንዲሁም የፒያኖ ተጫዋች የሆነውና ለረጅም አመታት በአሜሪካ በስደት የቆየው አንጋፋው ከያኒ፤ ከሙዚቃው ተራርቆ የከረመ ሲሆን ወደ ሙዚቃው የተመለሰው ከሁለት ዓመት ወዲህ መሆኑ ተገልጿል፡፡
በታዋቂው የሙዚቃ ሰው ፍራንሲስ ፋልሴቶ አነሳሽነት በግንቦት 2016 ፓሪስ በሚገኘው ‹‹ላ ኤሪ ቴጅ›› የተባለ ስቱዲዮ ግርማ በየነ ‹‹አካሌ ውቤ›› ከተሰኘው የኢትዮ ጃዝ ሙዚቃ ቡድን ጋር ‹‹ኢትዮፒክስ 30 ሚስቴክስ ኦን ፐርፐዝ›› የተሰኘውንና 14 ዘፈኖችን ያካተተው አልበሙን ያሳተመ ሲሆን፣ ባለፈው ማክሰኞ ያቀረበው ኮንሰርትም ይህንኑ አልበም ለማስተዋወቅ ያለመ እንደነበር ታውቋል፡፡ ለአርቲስቱ የመጀመሪያው ሙሉ አልበሙ ነው ተብሏል፡፡ ግርማ አልበሙን ለማስተዋወቅ ባዘጋጀው ኮንሰርት፤ ከ‹‹አካሌ ውቤ›› ባንድ ጋር አስደናቂ ትርኢት ያሳዩ ሲሆን በተለይ ግርማ በድምፅ ብቻ ሳይሆን በፒያኖ ችሎታውም ብዙዎችን አስደንቋል፡፡ አርቲስቱ በ1960ዎቹ፣ ከ60 በላይ የሙዚቃ ቅንብሮችን የሰራ ሲሆን ግሩም የግጥምና ዜማ ደራሲም ጭምር እንደነበር ይነገርለታል፡፡ በብሔራዊ ትያትር ቤት ባቀረበው ኮንሰርት ‹‹እንከን የሌለሽ››፣ ‹‹ካንቺ ወዲያ ሴት አላምንም››፣ ‹‹ፍቅር እንደክራር››፣ ‹‹ፅጌረዳ››፣ ‹‹መስሎን ነበር››፣ ‹‹ሙዚቃዊ ስልት›› የተሰኙትን ጨምሮ በርካታ ስራዎቹን በመጫወት አድናቆት የተቸረው ሲሆን ‹‹የድምፁ አለማርጀት›› ለብዙዎች መነጋገሪያ ሆኖ አምሽቷል፡፡ በኮንሰርቱ ላይ ስለፍቅር አብዝቶ የሰበከው ድምፃዊው፤ ከኢትዮጵያ ሴት ድምፃዊያን ሄለን በርኼ በተለይ ‹‹አታስፈራራኝ›› ለሚለው ዘፈኗ ያለውን አድናቆት በአደባባይ ገልጿል፡፡
ግርማ በየነ ከዚህ ቀደም ‹‹ዘራፍ››፣ ‹‹ጋይድ ቱ ሚዩዚክ ኦፍ ኢትዮጵያ››፣ እ.ኤ.አ በ2004 ‹‹በወርልድ ሚዩዚክ ጌት ወርክ›› አሳታሚነት ‹‹ኢትዮፒክስ ቁጥር 8››፣ ‹‹ስዊን ጊንግ አዲስ››፣ በቡዳ ሚዩዚክ አሳታሚነት ደግሞ ‹‹ኢትዮፒክስ 22›› በተሰኙ አልበሞች ላይ ተሳትፏል፡፡ አርቲስት ግርማን ያጀበው ‹‹አካሌ ውቤ›› የኢትዮ ጃዝ ሙዚቃ ቡድን፤ በፈረንሳይ ሙዚቀኞች የተደራጀ ሲሆን ከ74 በላይ የሙዚቃ ኮንሰርቶችን በዓለም ዙሪያ ማቅረቡ ታውቋል፡፡ ከወራት በፊትም በፈረንሣይ ከታዋቂው የፒያኖ ተጫዋች ሀይሉ መርጊያ ጋር በ ‹‹ስቱዲዩ ዴላ ኤል ሚቴጅ›› ታላቅ የሙዚቃ ዝግጅት ማቅረባቸው ተጠቁሟል፡፡