Administrator

Administrator

አገኘሁ_አዳነ_ድልነሣሁ-


በቤልጅዬም የኢትዮጵያ ኤምባሲ፣ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለ_የሥነጥበብና_ዲዛይን_ት_ቤት ጋር በመተባበር በቤልጅዬም ከየካቲት 18 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ የሥዕል ትርዒት አቅርበዋል። ይህ ኤግዚቢሽን መልኩና ፈርጁ ብዙ የሆነውን የዲፕሎማሲ ዓለም በሥነጥበብና ባህል ለማዋዛት፣ ነባሩ የሥነ ጥበብ ብሂል በዘመነኛው የሥነ ሥዕል እንቅስቃሴ ላይ ያሳደረውን ክንደ ብርቱ ተፅዕኖ ለማመላከትና ት/ቤቱ ከቀረው ዓለም አቻ ተቋማት ጋር ትስስር መፍጠር እንዲችል ታስቦ የተሰናዳ ነበር።  በትርዒቱ መክፈቻ የአውሮፓ ኅብረት የውጭ ግንኙነት  ቢሮ ዋና ፀሐፊ ስቴፋኖ ሳኒኖ (Stefano Sannino)፣ የቤልጂየም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተወካይ፣ አምባሳደር  ባርት ዴ ግሩፍ፣ የአካፓድ ምክትል ዋና ፀሐፊ ዶ/ር ኖርበርት ሪቻርድ ኢብራሂም፣ በብራስልስ የሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ አባላት የተገኙ ሲሆን፣ የሥነ ጥበብ ልሂቃንና የሥነ ጥበብ አፍቃርያን ታድመውበታል።
በቤልጅዬም የኢትዮጵያ ኤምባሲ ባለሙሉ ስልጣን እንደራሴ አምባሳደር ሒሩት ዘመነ፣ አምባሳደር ሞላልኝ አስፋው እና የሥራ ጓዶቻቸው ዝግጅቱ የተሳካ ይሆን ዘንድ የሚያስመካ ጥረት አድርገዋል። ጥረቱ ፍሬ አፍርቶም በቤልጅዬም የሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማህበረሰቡ፣ የታሪክ፣ የሂስ እና የሥነጥበብ ንድፈ ሐሳብ ልሂቃን በኤምባሲው እንዲሰበሰቡ ሆነዋል።
የአንትወርፕን (Antwerpen) Royal Academy of the Arts መምህራንም በኤምባሲው ተገኝተው ፍሬ ያለው ውይይት ማድረግ ችለናል። ምሑራኑ ትርዒቱን ተመልከተው መደነቃቸውን የገለጹልን ሲሆን፣  በምንተባበርባቸው ተቋማዊ የጋራ ጉዳዮች ላይ መክረናል።  
የቀረበው የሥዕል ትርዒት ተወዳጅነቱ ከፍ በማለቱ ምክንያት ለተጨማሪ አንድ ሳምንት የተራዘመ ሲሆን፣ ለአካባቢው ማኅበረሰብ መነቃቃት መፍጠሩን በዝግጅቱ አካል የሆንነው ሙያተኞች መታዘባችንን እንመሰክራለን።
ሀገራችን ኢትዮጵያ ከሌላው ዓለም ጋር የምትነጋገርበትን የቋንቋ አማራጭ ለማስፋት ሥነጥበብን ወደ ዲፕሎማሲው ዓለም የጋበዙትን አምባሳደር ሒሩት ዘመነን፣ አምባሳደር ሞላልኝ አስፋውንና የሥራ ጓዶቻቸውን  ማመስገን ይገባል።

ዳሸን ባንክ ሸሪክ የተሰኘ ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎት የጀመረበትን 6ኛ ዓመት ባከበረበት ዕለት ከደንበኞች በበጎ አደራጎት ፈንድ በአደራ የሰበሰበውን 12.5 ሚሊዮን ብር ለ18 አገር በቀል የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ለገሰ፡፡  

ዳሸን ባንክ በሚሰጠዉ ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎት ብቻ አሁን ላይ ከ1 ሚሊየን በላይ ደንበኞችን ማፍራት የቻለ ሲሆን፤ይህንንም በተለያዩ ስነ-ስርዓቶች አክብሯል፡፡

የዳሸን ባንክ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አስፋው ዓለሙ በስነ-ስርዓቱ ላይ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር፤ ለባንኩ አመኔታቸውን ለሰጡ ደንበኞች ከፍ ያለ ምስጋናቸውን አቅርበው፣ ወደፊትም ለላቀ ስኬት የሸሪዓህ መርህን በመከተል አዳዲስ የባንክ አገልግሎቶቸን እንደሚያቀርብ ገልፀዋል፡፡

አቶ አስፋው አክለውም፤ በአደራ የተሰጣቸውን ገንዘብ የተረከቡ 18 አገር በቀል በጎ አድራጎት ድርጅቶች የማህበረሰቡን ችግር ለመቅረፍ በሚያስችሉ ስራዎች ላይ እንዲያውሉት አደራ ብለዋል፡፡ በቀጣይም ባንኩ እነኚህንም ሆነ መሰል ሌሎች ተቋማትን የማህበረሰቡን ችግሮች በዘላቂነት በሚፈቱ ስራዎች ላይ በጋራ ለመስራት የሚሻ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

ዳሸን ባንክ፤ የካቲት 26 ቀን 2010 ዓ.ም በአንድ መስኮት መስጠት የጀመረው አገልግሎት አድጎ ዛሬ ላይ ከ70 በላይ ሙሉ በሙሉ ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት በሚሰጡ ቅርንጫፎች እንዲሁም ከ800 በላይ በሆኑ ቅርንጫፎች ደግሞ በመስኮት ለደንበኞቹ የተሟላ ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡ ከደንበኞቹም ከ9.5 ቢሊየን ብር በላይ ማሰባሰብ የቻለ ሲሆን፤ ከዚህም ውስጥ ከ6 ቢሊየን ብር በላይ በተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ ለተሰማሩ ደንበኞቹ ፋይናንስ አድርጓል፡፡

ባንኩ ከወለድ-ነፃ የባንክ አገልግሎት የሚጠይቀውን ሙያዊና ሸሪዓዊ ስነ-ምግባር ተግባራዊ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ በዚህም ረገድ እ.ኤ.አ ህዳር 28 ቀን 2023 በባህሬን ማናማ በተካሄደው 9ኛው የኢስላሚክ ሪቴል ባንክ ሽልማት ላይ ጠንካራው ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት በኢትዮጵያ የሚሰጥ ባንክ (The strongest Islamik Retail Banking Window in Ethiopia 2025) በሚል ተቀማጭነቱ ሎንዶን በሚገኘውና  በፋይናንስ ዘርፍ ጥናትና ምርምር በሚሰራዉ  ኬምብሪጅ አይ ኤፍ ኤ(Cambridge IFA) የተሰኘ ተቋም ሽልማት አግኝቷል፡፡ ባንኩን ለዚህ ሽልማት ካበቁት መሰፈርቶች አንዱ  ጠንካራ የሸሪዓህ አስተዳደር ማዕቀፍ በመተግበሩ ነው፡፡

ባንኩ በአለም አቀፍ ደረጃ የእስላማዊ ፋይናንስ ተቋማትን የሂሳብ፣ ኦዲትና ሸሪዓህ መስፈርቶችን የሚያወጣው ተቋም (AAOIFI) ቋሚ አባል የሆነ፣ በኢትዮጳያ ብቸኛው የፋይናንስ ተቋም መሆኑ ይታወቃል፡፡

በሙዚቃው ኢንዱስትሪ ውስጥ ከሚገኙ አለም አቀፍ ተቋማት ጋር  በጋራ እየሰራ የሚገኘው ሰዋሰው መልቲሚዲያ፣ በትውልደ ኢትዮጵያውያን በተመሰረተውና በተለያዩ የአሜሪካን ግዛቶች በስፋት በዲጂታል ማስታወቂያው ዘርፍ ላይ እየሰራ ከሚገኘው አድ ቴክ ሶሉሽን ጋር  በጋራ ለመስራት በዛሬው ዕለት ከስምምነት ላይ ደረሱ፡፡

የዛሬው ስምምነት ኢትዮጵያውያን አርቲስቶችን ወደ ዓለም አቀፉ የሙዚቃ ኢንዱስትሪ እንዲሁም በሙዚቃው ዘርፍ የተሰማሩ ግዙፍ አለም አቀፍ ተቋማትን ደግሞ ወደ ሀገራችን የኪነ-ጥበብ ዘርፍ ለማስገባት አልሞ ለሚሰራው  ሰዋሰው መልቲሚዲያ ወሳኝ ምዕራፍ ነው ተብሏል፡፡

በተለያዩ የአሜሪካን ግዛቶች በኢትዮጵያውያን በሚዘጋጁ ትልልቅ ፕሮግራሞች፣ በአብዛኞቹ የሀገሪቱ ግዛቶች በሚገኙ ሞሎች፣ አደባባዮች፣ ሆቴሎችና በርካታ ሰዎች በሚሰበሰቡባቸው ጎዳናዎች ላይ የዲጂታል ማስታወቂያ ስራን የሚሰራው አድ ቴክ ሶሉሽን፣ በሰዋሰው በኩል የሚወጡ አልበሞችን፣ የተለያዩ አርቲስቶችን ስራዎች እንዲሁም ከሰዋሰው ጋር በጋራ የሚሰሩ ተቋማትን አገልግሎቶች የሚያስተዋውቅ ይሆናል፡፡

የሰዋሰው ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ሀብቱ ነጋሽ፤ በመላው አለም የሰዋሰው አርቲስቶችንና ስራዎችን ለማስተዋወቅና ለማስፋፋት ከምናደርጋቸው ስራዎች መካከል ይህ አንደኛው መሆኑን ጠቅሰው፣ በስምምነቱም ደስተኛ መሆናቸውን ገልፃዋል፡፡

በኢትዮጵያ የአድ ቴክ ሶሉሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አማኑኤል ኪዳኔ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያን የሙዚቃ ኢንዱስትሪ በተለየ መልክ ለማሻሻልና ለመለወጥ ከሚሰራው ሰዋሰው ጋር በጋራ ለመስራት በመስማማታችን ከፍተኛ ደስታ ተሰምቶናል ብለዋል፡፡

ሁለቱ ድርጅቶች በቀጣይ በአውሮፓ የተለያዩ ሀገራት በጋራ የመስራት ውጥን እንዳላቸውም ተጠቁሟል፡፡

የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ፕሮጀክት አፈፃፀም 95 በመቶ መድረሱን የሕዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ፕሮጀክት ጽ/ቤት ገለጸ።

ማስተባበሪያ ፕሮጀክት ጽ/ቤቱ  በዛሬው ዕለት በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተነገረው፤ የሲቪል ሥራው 98 በመቶ እንዲሁም የኤሌክትሮሜካኒካል ሥራው 78 በመቶ ደርሷል፡፡

ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታው አሁን ላይ 95 በመቶ የደረሰ ሲሆን፤ ሀይል የማመንጨት ምዕራፍ ላይም ይገኛል።

መላ የኢትዮጵያ ህዝብ ካለው ላይ በማዋጣት ግድቡን  ለዚህ እንዳደረሰው ያመለከተው ጽ/ቤቱ፤ በ13 አመታት ውስጥም ከ18.9 ቢሊዮን ብር በላይ ማሰባሰብ ተችሏል ብሏል።
 
ግድቡ አሁንም ከፍጻሜው እስኪደርስ ህዝቡ የሚያደርገውን ርብርብ እንዲያጠናከር ጽ/ቤቱ ጥሪ ቀርቧል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ  የኤሌክትሪክ ሀይል ማመንጫ ግድብ የመሰረት ድንጋይ የተቀመጠበትን 13ኛ ዓመት በተለያዩ ዝግጅቶች ለማክበር መዘጋጀቱን የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ፕሮጀክት ጽ/ቤት አስታውቋል፡፡


   የቴሌግራም ቻናልችንን  በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
https://t.me/AdissAdmas

• ቅዱሳት መጻሕፍት በቅናሽ ዋጋ ለምእመናን ይቀርባሉ ተብሏል
“መጽሐፍ ቅዱሳዊ እሴቶችን በሕዝባችን ሕይወት እናሥርጽ!” በሚል መሪ ቃል፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ሳምንትና የቅዱሳት መጻሕፍት ዐውደ ርዕይ ከመጋቢት 16 እስከ መጋቢት 21 ቀን 2016 ዓ.ም በሀገር አቀፍ ደረጃ በአዲስ አበባ ስካይ ላይት ሆቴል እንደሚካሄድ ተገለጸ፡፡
የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኀበር በዛሬው ዕለት ጠዋት በስካይ ላይት ሆቴል በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፤ የመጽሐፍ ቅዱስ ሳምንት ለአምስት ቀናት እንደሚካሄድ አስታውቋል።
በዚህ መርሐ ግብር ላይ የኢትዮጵያ አርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፣ የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ፣ የወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት ፣ ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ተቋማትና በርካታ ቁጥር ያላቸው ምእመናን በስፋት እንደሚሳተፉበት ተነግሯል፡፡
98 ዓመት እድሜ ያስቆጠረው የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኀበር ሰብሳቢ ዶ/ር ተስፋጽዮን ደለለው እንደገለጹት፤ ማኀበሩ 22 በሚደርሱ የኢትዮጵያ ቋንቋዎች መጽሐፍ ቅዱስ በማስተርጎም ላይ ሲሆን በቀጣይ ከ20 በላይ በሚደርሱ ተጨማሪ ቋንቋዎች አስተርጉሞ ለማቅረብ በዝግጅት ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
በአውደ ርዕዩ ላይ ቅዱሳት መጻሕፍት በቅናሽ ዋጋ ለምእመናን እንደሚቀርቡ የተገለጸ ሲሆን፤ ምዕመናን በተጠቀሱት ቀናት ያለምንም ክፍያ ወደ ስካይ ላይት ሆቴል በመምጣት በስጋም በነፍስም ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማህበሩ ጥሪ አቅርቧል።
በመርሐ ግብሩ ማጠናቀቂያ መጋቢት 21 ቀን 2016 ዓ.ም የመጽሐፍ ቅዱስ ቀን በሚል የእውቅና እና የምስጋና ፕሮግራም መዘጋጀቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡

   የቴሌግራም ቻናልችንን  በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
https://t.me/AdissAdmas


የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባህል ኪነጥበብና ቱሪዝም ቢሮ ዘንድሮ ባዘጋጀው የ"ዝክረ ኪነጥበብ" መርሃ ግብር፣ የበርካታ ቴአትሮች ደራሲ የሆነው ፀሐፌ ተውኔት ውድነህ ክፍሌ የክብር ዲፕሎማና እውቅና ዛሬ የካቲት 26 ቀን 2016 ዓ.ም በሀገር ፍቅር ቴአትር ቤት ተበርክቶለታል።

ጸሃፌ ተውኔት ውድነህ ክፍሌ፤  ግማሽ ጨረቃ፣ የደፈረሱ አይኖች፣ ባቢሎን በሳሎን ፣ ቅጥልጥል ኮከቦች፣ የሌሊት ሙሽሮች፣ ንጋት ፣ የሌሊት ጧፍ፣ ሦስቱ ሰዎች፣ የቼዝ አለም ፣ ቤርሙዳ እና ሌሎች የመድረክና የስክሪን ድራማዎች ደራሲ መሆኑ ይታወቃል፡፡

በእውቅናው ሥነሥርዓት ላይም በፀሐፌ ተውኔት ውድነህ ክፍሌ ላይ የሚያጠነጥን  ዘጋቢ ፊልም፣ በተውኔቶቹ ላይ የባለሞያ ዳሰሳና ከ“የደፈረሱ ዓይኖች” ቴአትር ላይ ቅንጫቢ ተውኔት ቀርቧል።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባህል ኪነጥበብና ቱሪዝም ቢሮ በየዓመቱ በሚያዘጋጀው "ዝክረ ኪነጥበብ" ልዩ መርሃ ግብር፣ ለሀገራቸው ኪነጥበብ በሙያቸው የላቀ አስተዋጽኦ ካበረከቱ ጠቢባን  አንዱን በመምረጥ የክብር ዲፕሎማና እውቅና ሲሰጥ ቆይቷል::

በቢጂአይ ኢትዮጵያ እና በፐርፐዝ ብላክ ኢትዮጵያ መካከል ሲካሄድ የቆየው ሜክሲኮ የሚገኘው የቢጂአይ ኢትዮጵያ ዋና መሥሪያ ቤት ህንፃ ሽያጭ ድርድር፣ ውል ለማሰር ባለመቻሉ ሂደቱ መቋረጡ ተገልጧል፡፡

ቢጂአይ ኢትዮጵያ ትላንት ባሰራጨው መግለጫ፣  የሽያጩ ውል የተቋረጠው ፤ በፐርፐዝ ብላክ ኢትዮጵያ  በኩል ግብይቱን ለማጠናቀቅና የሽያጭ ውሉን ለመፈረም ፍላጎትና ቁርጠኝነት ባለመኖሩ ነው፤ ብሏል።

ፐርፐዝ ብላክ ኢትዮጵያ ግን በዚህ አይስማማም፡፡ ኩባንያው ዛሬ ጠዋት ሠንጋ ተራ በሚገኘው የዋና መ/ቤቱ አዳራሽ በሰጠው መግለጫ፤ ”ቢጂአይ ኢትዮጵያ የመንግሥት ግዴታዎችን ባለመወጣቱ በውልና ማስረጃ ለመፈራረም አልተቻለም“ ብሏል፡፡

ለቢጂአይ 1ቢ. 150 ሚሊዮን ብር ክፍያ መፈጸሙን ያስታወሰው ፐርፐዝ ብላክ፤ ቀሪውን ክፍያ በህጉ መሰረት  በውልና ማስረጃ ስንፈራረም ለመክፈል ዝግጁ ነን ብሏል፡፡

”ከታክስ ነጻ የሆኑበት ወረቀት ከቀረበ በውልና ማስረጃ እንፈራረማለን፤ እኛ ተገቢውን ሰነድ ካሟሉ በሁለተኛው ዙር የሚጠበቅብንን 2.5 ቢሊዮን ብር ለመክፈል ዝግጁ ነን፡፡“ ብሏል፤ ፐርፐዝ ብላክ በሰጠው መግለጫ፡፡

ቢጂአይ ኢትዮጵያ የታክስ ክሊራንስ አቅርቦ በውልና ማስረጃ የማይፈራረም ከሆነ ግን ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት ለመውሰድ እንገደዳለን ብሏል - ፐርፐዝ ብላክ ኢትዮጵያ፡፡

ቢጂአይ እና ፐርፐዝ ብላክ ሜክሲኮ የሚገኘውን የቢጂአይ ኢትዮጵያ ዋና መ/ቤት ህንጻ ለመገበያየት የተዋዋሉት በ5 ቢሊዮን ብር ሲሆን፤ 1 ቢሊዮን ብር የቅድምያ ክፍያ መፈጸሙ ታውቋል፡፡ ከፐርፐዝ ብላክ ኢትዮጵያ የሚጠበቀው ሁለተኛ ክፍያ 2.5 ቢሊዮን ብር ሲሆን፤ ይህ ክፍያ የሚፈጸመው በውልና ማስረጃ ስንፈራረም ነው ብሏል - ፐርፐዝ ብላክ በመግለጫው፡፡

የፐርፐዝ ብላክ ኢትዮጵያ መሥራችና ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር ፍስሃ እሸቱ ለሥራ ጉዳይ በአሜሪካ እንደሚገኙና ከነገ ወዲያ ሐሙስ እንደሚመለሱ የተጠቆመ ሲሆን፤ አርብ ጠዋት በጉዳዩ ዙሪያ ዝርዝር መግለጫ ይሰጣሉ ተብሏል፡፡

ዝግጅት ክፍሉ በሁለቱም ወገን ያለውን ዝርዝር ጉዳይ እየተከታተለ ያደርሳችኋል፡፡

እየተገለማመጠ ሀኪሙን ተጠጋው። እምባ ያቆሩ አይኖቹን ጨመቅ፣ጨመቅ እያደረገ ወደ ጆሮው ጠጋ አለና፤ “ዶክተር የማሳክምበት አቅሙ የለኝም። እሱም አይድንም። ለስቃይና ለጭንቀት ከምንዳረግ እባክህ ሞቱን አፍጥንልኝ! ግደልልኝ!”
ዶክተሩ ጭንቅላቱን የተመታ ያህል ክው ብሎ በቆመበት ደርቆ ቀረ።
***
(ው.ክ)
ማስታወሻ፦ አንድ የህክምና ዶክተር የገጠመውን ከነገረኝ ተነስቼ ነው።

ማንይንገረው ሸንቁጥ

ሀብታሙ አለባቸው ቀደም ባሉ ጊዜያት አውሮራ፣ የሱፍ አበባ፣ የቄሳር እንባ፣ አንፋሮ፣ ህንፍሽፍሽ የተባሉ የአገራችን ታሪክና ፖለቲካ ላይ ያጠነጠኑ ልብ ወለድ መጻሕፍትን አበርክቶልናል፡፡ ከዚህ በተጓዳኝም “ታላቁ ተቃርኖ” በሚል ርዕስ አንድ ኢ-ልብወለዳዊ መጽሐፍ ለገበያ አቅርቧል፡፡ በዚህ ኢ-ልብወለዳዊ መጽሐፉ ውስጥ የሚከተሉት ሃሳቦች ይገኙበታል፡፡
““ብሔር ግንባታ”  ከሐገረ መንግሥት ምሥረታ  የሚቀጥል የተለየ ሌላ ሂደት ወይም ተግባር ነው፡፡……… ከሐገረ መንግሥት ምሥረታው ተግባር መጠናቀቅ በኋላ ወዲያውኑ ተከትሎ የሚመጣና ለረጅም ጊዜ የሚቀጥል ተግባር ነው፡፡ የዚህኛው ተግባር ቀጥተኛ ዒላማ፣ የአገር ግዛትና ሉዓላዊነት ሳይሆን ህዝቡ ነው፡፡ የቋንቋ፣ የሃይማኖት፣ የአካባቢ ወይም የመልክዓ ምድር፣ የሐብትና ገቢ መጠን ወይም ሌላ ልዩነት ተመልሶ ለሐገረ መንግሥቱ ህልውና አደገኛ እንዳይሆን አድርጎ ማስተሳሰር ግቡ ነው፡፡” (ገፅ 43) ”የብሔር ግንባታ የትም ዓለም ላይ በበርካታ ምክንያቶች አስቸጋሪ ተግባር ነው፡፡ የሚፈልገው የጥንቃቄ ደረጃም ከፍተኛ ነው፡፡ በየትኛውም መንገድና ዘዴ የተመሠረተ ሐገረ-መንግሥት በብሔር ግንባታ ሂደት ወቅት በሚሠራ ሥህተት ተመልሶ ሊፈርስ ይችላል፡፡”(ገፅ 135) በማለት ይቀጥልና ወረድ ብሎ፣ መንፈሳዊና ቁሳዊ የጋራ ቅርስና ስለ ቅርሱ የተያዘ የጋራ “ጥሩ ወይም መጥፎ ትዝታ” የተፈጠረበት አገራዊ ወይም ብሔራዊ ሁኔታ ለብሔር ግንባታ ወሳኝ ስለመሆኑ ከምሁራን ጽሑፍ ያጣቅሳል፡፡ ይህ የጋራ ቅርስና ትዝታም በትውልዶች ላይ ተፅዕኖ ሊያሳድር የሚችል የቀደመ ጊዜ የጋራ ስኬት ወይም ውድቀት ታሪክ ሊሆን እንደሚችልና ይህንን መሰል ታሪካዊ የትስስር ስኬት ወይም ውድቀት ያለበትን ትዝታና ቅርስ ምሁራን ”ዘ ፎረም ሮማነም“ ብለው ማተታቸውን ይነግረናል፡፡  ቅርሶቹ በህዝቦች መካከል የነበረውን ፍቅር ብቻ ሳይሆን ግጭቶቻቸውንም የሚያስታውሱ በመሆናቸው፣ ስለቅርሶቹ ምንነት እየጠየቀና እየተረዳ ያደገ ህጻን፣ የቆየ ግጭትን ከቂም በቀል በራቀ መልኩ በማስተዋል፣ ግጭትን እየፈቱና እየተማማሩ አብሮ መኖርን እሴት አድርጎ እንዲወርሰው ምክንያት እንደሚሆንለት ያብራራል፡፡
ይህንኑ ሃሳብ ወደኛ ያመጣውና “ዘ ፎረም ኢትዮጵያነም” ብለን ልንሰይመው እንደምንችል ጠቅሶ አቻ ትርጉሙን፣ “አጥንትና ጉልጥምት ኢትዮጵያ” በማለት አሥፍሮታል፡፡ “ስያሜውና አተረጓጎሙ አንድ ህዝብና ግለሰብ አባላቱ እንዴት በተቃራኒ መንገዶች አልፈው ለዛሬው አብሮነታቸው እንደደረሱ የሚናገርና በልዩ ልዩ መንገዶች የሚገለጽ ታሪካዊ የቅርሶችና የትዝታዎች ሰነድ ነው” ይለናል በገፅ 136፡፡
ለእኛ አገር ሁኔታ ጽንሰ ሃሳቡን ስንጠቀም መጠንቀቅ እንደሚገባን እያስጠነቀቀ፣ ”ጉልጥምት ኢትዮጵያ“ በርካታ ልዩነት ፈጥረው ወደ ግጭት ሊያመሩ የሚችሉ የፖሊሲና አስተዳደራዊ ስህተቶችን ተሻግሮ፣ ከፍ ባለ የማጣመርና ማቀናጀት ብቃቱ፣ የተለያዩ ፍላጎቶችንና ግፊቶችን የሚያስተሳስር ውጤታማ መረብ መሆኑን ያስረዳናል፡፡ ከዚህ አለፍ ብሎም፣ “አጥንትና ጉልጥምት ኢትዮጵያ” ትናንት ስለመሠራቱ ብንጠራጠር እንኳን፣ ቁርጠኝነቱ ካለ ዛሬና አሁን መፍጠር እንደሚቻልም ይነግረናል፡፡  ”የብሔረ- ኢትዮጵያ ግንባታ“ ማለትም ከዚህ የተለየ ትርጉም እንደሌለው በአፅንዖት አሥፍሯል፡፡ከላይ እንደተጠቀሰው፣ ደራሲው በኢ-ልብወለድ መጽሐፉ በግልፅ ያስቀመጠውን የ”አጥንትና ጉልጥምት“ ፅንሰ ሃሳብ፣ ለዚህ ልብወለዱ ዋነኛ ጭብጥ አድርጎ ብቅ ብሏል፡፡ ”አጥንትና ጉልጥምት“ ከሚለው ፅንሰ ሃሳብ የተቀዳው፣“ጉልጥምት ኢትዮጵያ” በሚል ርዕስ የተሰናዳው ልብወለድ፣ በገፀ ባህርያት ሥጋን ተላብሶ በመቅረቡ፣ ፅንሰ ሃሳቡን የዕለት ተለት ኑሮዋችን ውስጥ እንድንፈልገው፣ እንድናሰላስለው ይጎተጉተናል፡፡ ሴራውን በደህንነት መሥሪያ ቤት ክንውን ውስጥ ማዋቀሩ፣ የአገር ጉዳይ ከሥርዓት ባሻገር መታየቱን ያጎላል፡፡ አለፍ ሲልም፣ በአገራችን ነባራዊ ሁኔታ ወቅታዊ ቅራኔዎቻችንና እነሱን ልንፈታ የምንዳክርበት መንገድ፣ ምን ያህል ከትልቁ ስዕል የራቀ ስለመሆኑ እንድናስብ ምክንያት ለማግኘት ያግዘናል፡፡
እርግጥ ነው፣ ታሪኩ ልባችንን አንጠልጥሎ በውብ ቃላት ይፈሳል፡፡ ሁነቶችና ምናባዊ ቦታዎችን የሚገልጹት ቃላት ምስል ከሳች ናቸው፡፡ እንደዚያ ብቻ ግን አይደለም፣ በገፀባህሪያቱ በኩል በድፍረት የሚነሱት ሃይማኖታዊ፣ ፖለቲካዊና ታሪክ ነክ ሃሳቦች ቆም ብለን እንድናሰላስል የሚያስገድዱን ናቸው፡፡ ደራሲው፣ ሀብታሙ አለባቸው  ሃሳብ የማይነጥፍበት ደፋር ደራሲ መሆኑን በዚህም ድርሰቱ አስመስክሯል፡፡
ፖለቲካን ያለሙያ እንደልባቸው ‘የሚተነትኑ ጎበዛዝት’ በበዙበት ዘመን፣ የፖለቲካ ምሁሩ ሀብታሙ አለባቸው፣ ፖለቲካና  ታሪካችንን በልብወለድ መልክ ማስኮምኮሙን የተጋበት ምስጢር ምንድን ነው? ብለን ስንጠይቅ፣ አንድ ዘመን አይሽሬ ግሪካዊ ጸሐፊ ፊታችን መጥቶ ድቅን ይላል - ኒኮስ ካዛንታዝኪስ።
የሕይወት ትርጉም ለጠፋበት፣ ተቅበዝባዥ የሃያኛው ክፍለ ዘመን ሰው፣ አዲስ አለም ሊፈጥሩለት ተፍተፍ ይሉ በነበሩት ማርክሲስቶች ሃሳብ፣ ካዛንታዝኪስ ተማረከ። የጦፈ ወዳጅነትም መሠረተ። ቭላድሚር ኤሊች ሌኒንንም፣ ከሰማይ እንደወረደ መና ቆጠረው።  ትግሉን ለማገዝም አራት ያህል ጊዜ ወደ ሶቪየት ህብረት ተመላለሰ። በመጨረሻ ጉዞው የሶቪየት ህብረት መንግሥት ዕድል ሰጥቶት፣ አገሪቱን ከጫፍ ጫፍ ዞሮ በመጎብኘት ስለ አዲሱ መሲህ/አዳኝ- ኮሚኒዝም፣ ሊጽፍ ተነሳሳ። ጉብኝቱን ሲያጠናቅቅ ግን ያየውንና የሰማውን ሁሉ በፕሮፓጋንዳ መልክ መጻፍ እርባና እንደሌለው ተገለጠለት። በተመስጦ የተቀበለው ማርክሲዝም ብቻውን፣ የሰው ልጆችን መንፈሳዊ ጉድለት ለመሙላት በቂ እንዳልሆነ ተገነዘበ። እናም የፈጠራ ድርሰትን ሙጥኝ አለ።
የኛው ደራሲ ሀብታሙ አለባቸውስ?
የፖለቲካ ሳይንስ ተምሯል፣ አስተምሯል። በመስኩ የተለያዩ ጽሑፎችንና መጽሐፍም አበርክቷል። አለፍ ሲልም ከፍተኛ በሚባል የመንግሥት አስተዳደር ባለሥልጣን ሆኖ አገልግሏል።
“በሙያህ የፖለቲካ ጽሑፎች ላይ ከማተኮር ይልቅ ለምን ወደ ፈጠራ ድርሰት አጋደልክ?” ብለው ጋዜጠኞች እንዳይጠይቁት፣ እስካሁን ለሚዲያ ቅርብ እንዳልሆነ አውቀናል። የግሪኩን ጠሃፊ ቀደም ብለን የጠቀስነው አመሳስሎ ለመገመት እንዲመቸን ስለሆነ፣ ሀብታሙ አደባባይ ወጥቶ፣ የራሱን ሃቅ እስኪያጋራን ድረስ፣ እንደፈረደብን እንገምታለን -  ”የፈጠራ ድርሰት “ጉልጥምት ኢትዮጵያን” ለማጠናከር ትልቁ መሣሪያዬ ነው” የሚል ይመስለኛል። ቢልም ያምርበታል!!!


የይሓ ቤተ መቅደስ አስደናቂ ቅርስ ነው። ከዚሁ አጠገብ ሌላ ሕንጻ በጥንት ዘመን ተገንብቶ እንደነበር የፍርስራሽ ምልክቶች ይጠቁማሉ። ነገር ግን፣ በቂ ምርምር ሳይካሄድበት እስከ 2009 ድረስ ቆይቷል።
ቀደም ሲል በተደረጉ አነስተኛ ጥናቶች አማካኝነት የተወሰኑ መረጃዎች መገኘታቸው ግን አልቀረም። እንዲያም ሆኖ፣ የይሓ ግንባታ በየመን አገር ከሚገኙ ጥንታዊ ሕንጻዎች ጋር ይመሳሰላል በማለት ነበር የቅርስነቱን ለመግለጽ የሚሞክሩት።
የይሓ ሕንጻ ግን ከተገመተው በላይ ሆኖ ነው የተገኘው። ባለፉት ዐሥር ዓመታት በተካሄዱ ጥናቶች አማካኝነት የተገኙ መረጃዎች… የይሓ ሕንጻ በግዝፈቱም በአሠራር ጥበቡም በዘመኑ አቻ እንዳልነበረው ያረጋግጣሉ ተብሏል።
ጥንታዊነቱም ከእስካሁኖቹ እንደሚቀድም ተጠቅሷል። ከ2800 ዓመት በፊት የተገነባ ነውና።
ምንም እንኳ የጥናቱ ውጥን፣ “ከየመን ጥንታዊ ሕንጻዎች የተኮረጀ” እንደሆነ በመገመት የተጀመረ ቢሆንም፣ በቁፋሮ የተገኙ የሕንጻው የግንባታ ቁሳቁስ ሲታዩ ግን፣ በዐይነታቸውና በመጠናቸው እንዲሁም በአሠራር ጥበባቸው እጅግ የላቁ ሆነው ተገኝተዋል።
እናም፣ የይሓ ሕንጻ የቅርስነት ክብር ከየመን ግንባታዎች ጋር ስለተዛመደ አይደለም ተብሎ ተነገረለት። ራሱን የቻለ ትልቅ ግኝት እንደሆነም ታመነበት።
የዚህን ግኝት ግዙፍነትና ጥንታዊነት ለመገንዘብ፣ ከዝነኛው የይሓ ቤተ መቅደስ ጋር በማነጻጸር ብናየው ሳይሻል አይቀርም።
በጥበብ የተራቀቀው የይሓ ቤተ መቅደስ!
የይሓ ቤተ መቅደስ የዛሬ 2500 ዓመት ገደማ የተገነባ ሳይሆን አይቀርም ተብሎ ነበር የተገመተው። አለምክንያት አይደለም። በየመን ከሚገኙ ተመሳሳይ ግንባታዎች በፊት የኢትዮጵያ ሊቀድም አይችልም ከሚል ሐሳብ ጋር ተያይዞ የመጣ ግምት ነው።
በደንብ ከተጠና በኋላ ግን፣ የሕንጻው ዕድሜ ከተገመተው በላይ እንደሆነ ታውቋል። የይሓ ቤተ መቅደስ 2800 ዓመት ያስቆጠረ ታሪከኛ ቅርስ እንደሆነ ታምኖበታል ብለዋል ታዋቂው የአፍሪካ የቅርስ ተመራማሪ ዴቪድ ፍሊፕሰን።
Epigraphic comparisons… suggested a date for the Great Temple no earlier than 500 BC, but more recent views on the chronology of southern Arabian epigraphy and architecture favour an age some three centuries earlier. (Foundations of an African Civilisation (AKSUM & THE NORTHERN HORN), David W. Phillipson, 2012. ገጽ 26)።
ታዲያ የኢትዮጵያ የሥልጣኔ ታሪክ እያደር ይደምቃል ቢባል ይበዛበታል?
18.6 ሜትር በ15 ሜትር ስፋት ያለውና በ14 ሜትር ቁመት የተገነባው ቤተ መቅደስ፣ በአምስት ምሶሶዎች ላይ የቆመ ደጀ ሰላም የተሰራለት ጥንታዊ ግንባታ ነው። ቤተ መቅደሱና ደጀ ሰላሙ፣ በጥበብ የተራቀቀ አስደናቂ የሥልጣኔ ቅርስ እንደሆነ ምንም አያጠራጥርም።
የቅርስ ተመራማሪዎች ብቻ ሳይሆኑ መንገደኛ ተመልካቾችም የሕንጻውን ጥበብ በቀላሉ አይተው ሊመሰክሩ ይችላሉ። እጅግ በተራቀቀ ጥበብ እንደተገነባ  ከፍሊፕሰን አገላለጽ መረዳት ይቻላል። “built of large, extremely finely dressed, rectangular blocks  of silicified sandstone” በማለት ጽፈውለታል።
የይሓ ቤተ መቅደስ ያን ሁሉ ዘመን ተሻግሮ እስከ ዛሬ የዘለቀው በግንባታው ጥበብና በአናጺዎቹ የሙያ ልሕቀት እንደሆነ ሌሎች አጥኚዎችም ተናግረዋል።
እናም፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ ክብሩ እየተገለጠ በአድናቆት ሰማይ የነካው የይሓ ቤተ መቅደስ፣ ከአጠገቡ ሌላ ተፎካካሪ ቅርስ ይመጣለታል ወይም ይመጣበታል ተብሎ አልተገመተም ነበር።
ግን እንደተገመተው አልሆነም፤ ከተገመተው በላይ እንጂ።
ከአጠገቡ ሌላ አንጋፋ ቅርስ ተገኝቶለታል። “ግራት በዓል ገብሪ” ይሉታል - ቦታውን። ጥንታዊ ግዙፍ ሕንጻ ከ2800 ዓመት በፊት ተገንብቶ የነበረው እዚህ ቦታ ላይ ነው ብለዋል የቅርስ ተመራረማሪዎች።
ሕንጻው 60 ሜትር በ50 ሜትር ስፋት አለው። ባለደረጃ መድረክ ላይ የተሠራ ይመስላል።
መድረኩ የስድስት ሜትር ቁመት አለው። እዚያ ላይ ነው ሕንጻው የሚጀምረው።
ከፊት ለፊት የሕንጻው መግቢያ በስድስት ግዙፍ ምሶሶዎች ጸንቶ የቆመና ግርማ ሞገስን የተላበሰ ነው። ምሶሶዎቹ 10.5 ሜትር ርዝመት እንደነበራቸው አጥኚዎቹ ይገልጻሉ። ውፍረታቸው ደግሞ 85 ሴንቲሜትር በ95 ሴንቲሜትር ነው።
የአንዱ ምሶሶ ክብደት፣ ከ200 ኩንታል ይበልጣል።
የሕንጻው የግድግዳ ውፍረት 2 ሜትር ገደማ ነው።
የምሶሶዎች ትልቅነትና የግድግዳው ውፍረት ከህንጻው ግዙፍነት ጋር የተያያዘ እንደሆነ ተመራማሪዎች ይናገራሉ፡፡ (Journal of Architectural Engineering Technology፣ Published: 29-May-2023፣ Volume 12 Issue 4፣ Preliminary Structural Analysis for the Archaeological Reconstruction of the Ancient Palace Grat Be’al Gibri in Yeha, Ethiopia)
በቁፋሮ የተገኙትን መረጃዎች የመረመሩ አንጥኚዎች እንደሚሉት ከሆነ፣ ሕንጻው ከአምስት እስከ ዘጠኝ የሚደርስ ፎቅ ነበረው። የሕንጻው መልክና ቅርጽ ምን እንደሚመስል ለማሳየትም የምስል ንድፍ አቅርበዋል።  
ይህም ብቻ አይደለም።
የእስካሁኑ የቁፋሮ ግኝት አስደናቂ ቢሆንም፣ ያለ ቁፋሮ በማግኔቲክ ዘዴ በዙሪያው የተደረጉ የቅኝት ጥናቶች ደግሞ ሌላ ተጨማሪ መረጃ ይዘው መጥተዋል። በቁፋሮ የተገኘው ጥንታዊ የሥልጣኔ ቅርስ ቀላል ባይሆንም፣ ገና በቁፋሮ ያልተገለጠው ጥንታዊ ግንባታና ቅርስ እንደሚበልጥ ተመራማሪዎች ተናግረዋል። ለቁፋሮም ጓጉተዋል።
በእርግጥ የቁፋሮ ጥናት ለማካሄድ ገና ብዙ ውጣውረድ እንደሚኖር ያውቃሉ። አካባቢው ላይ የመኪና መንገድ ለመሥራትና የአውቶቡስ መነሃሪያ ለመገንባት እንደታሰበ ሰምተዋል።
ለእነዚህ ሥራዎች አማራጭ ቦታ ካልተገኘላቸው ለቅርሶች አደጋ ነው፤ ለምርምርም እንቅፋት ነው።
ሌላው ችግርስ ምንድነው?
ትልቁ ችግር ጦርነት ነው። በጀርመንና በኢትዮጵያውያን ተመራማሪዎች ከ2009 እስከ 2020 ሲካሄድ የነበረው ጥናት በጦርነት ምክንያት ለረዥም ጊዜ ተቋርጧል። በቅርቡ ወደ ጥናታቸው ለመመለስ እየሞከሩ እንደሆነ ቢገለጹም፣ ወደ ሥራ ለመመለስም ራሱን የቻለ ትንሽ “ጥናት” ማካሄድ፣ የቅድመ ዝግጅት “ሥራ” ማከናወን የግድ ነው።
ምን ለማለት ፈልጌ ነው? ከጥንታዊ ሥልጣኔና ከአስደናቂ ቅርሶች ጋር ተያይዞ፣ ባለፉት ሁለት ሦስት ዓመታት የምንሰማው ወሬ፣ ከጦርነት አደጋና ጦስ ጋር እየተዛመደ ነው። ከእንደዚህ ዐይነት የጦርነት አደጋና ጦስ ተገላግለን የምናየው መቼ ይሆን?
በሥዕል ያጌጡ የሃይማኖት መጻሕፍት በአባ ገሪማ ገዳም  
ከመቶ ዓመት በፊት የእንግሊዝ ሙዝዬም የቅርሶች የበላይ ጠባቂ የነበሩት ወሊስ በጅ፣ በዘመናቸው ከሚጠቀሱ የቅርስ ምሁራ መካከል ቀዳሚ ባለዝና ናቸው። ጥንታዊ የኢትዮጵያ ድርሳናትንና መዛግብትን ተርጉመው አሳትመዋል። የነገሥታት የዜና መዋዕል ድርሳናትን በማሰባሰብና በማጠናቀር በእንግሊዝኛ ሁለት ዳጎስ ያሉ መጻህፍት አበርክተዋል። ክብረነገሥት የተሠኘውንም መጽሐፍ ከግዕዝ ወደ እንግሊዝኛ ተርጉመዋል።
ሰውዬው እንዴት ጊዜ እንደሚበቃቸው ባይታወቅም፣ በጥንት በባቢሎን ቋንቋ የተጻፉ መዛግብትንም ተርጉመዋል። የባቢሎን ቅርሶችን የሚዳስስ መጽሐፍም አሳትመዋል። ምን ይሄ ብቻ!
የግብፅ ጥንታዊ ጽሑፎች በብዛት ወደ እንግሊዝኛ ተርጉመዋል፡፡ በጥንታዊ የግብፅ ሃይማኖትና እምነት ዙሪያ፣ በርካታ መጻሕፍትን ለንባብ አብቅተዋል።
እንዲያውም፣ የግብፅ ጥንታዊ ቋንቋና አጻጻፍ ላይ የመጀመሪያውን መዝገበ ቃላት አዘጋጅተው ለታሪክ ተመራማሪዎች አቅርበዋል - በ1500 ገጽ።
በአጠቃላይ፣ ከ25 በላይ ግዙፍ መጻሕፍት በወሊስ በጅ ተዘጋጅተው ታትመዋል።
የሆነ ሆኖ እኚሁ ዝነኛ የእንግሊዝ ሙዚዬም ኀላፊ የኢትዮጵያን ታሪክን በሚመለከት የዛሬ 95 ዓመት ባሳተሟቸው ሁለት መጻሕፍት ላይ፣ ጥንታዊ የግዕዝ ድርሳናትንና መዛግብትን እየዘረዘሩ አብራርተዋል።
በብራና ላይ የተጻፉ መዛግብት በዘመን ብዛት ከአገልግሎት ውጭ እንደሚሆኑ በመግለጽ፣ በዚህም ብዙ የኢትዮጵያ ቅርሶች ጠፍተዋል በማለት ሐዘናቸውን ገልጸዋል።
እንዲያም ሆኖ እጅግ የሚያስደንቁና በጥበብ የተጻፉ የግዕዝ መጻሕፍት በየቦታው እየተገኙ የተመራማሪዎችን ቀልብ እንደማረኩ ወሊስ በጅ ገልጸዋል፡፡ በተለያዩ ገዳት ውስጥ የውጭ ሰው ያላያቸው በርካታ መጽህፍት እንደሚኖሩ አልጠራጠርም ሲሉም ጽፈዋል።በዚሁ አጋጣሚም ነው፣ በሥዕል ያጌጡ የሃይማኖት መጻሕፍት ላይ አስተያየታቸውን የሰጡት።በግዕዝ የተጻፉና በሥዕል ያጌጡ የሃይማኖት መጻሕፍት (illuminated manuscripts)  በኢትዮጵያ መኖራቸውን ሲገልጹ፣ ከ16 ክፍለ ዘመን ወዲህ የአውሮፖ መጻሕፍትን በማየት እንደተጀመረ ተናግረዋል።
As soon as the Abyssinians became acquainted with the Portuguese and Italian missionaries in the 16th century they discovered the existence of illuminated Books… and in the 17th century the native scribes and artists began to decorate their manuscripts with coloured pictures.
በሥዕል ያጌጡ የሃይማኖት መጻሕፍት በኢትዮጵያ የተዘጋጁት ከ1500 ወዲህ ከአውሮፓውያን በመኮረጅ ነው ሲሉ ዕውቁ ተመራማሪ ግምታቸውን ቢናገሩ አይገርምም፡፡
 ሌላ አማራጭ አልታያቸውም፡፡ ነገር ግን፣ ግምታቸውን እንደ እርግጠኛ ዕውቀት የቆጠሩት ይመስላል፡፡
ለነገሩ፣ ለበርካታ ዓመታት ይህን ግምታዊ ድምዳሜ የሚያፈርስ የጥናት ግኝት ጎልቶና ጎልምሶ አልወጣም፡፡ የድምዳሜያቸው ግን ትክክል አልነበረም፡፡
ዋሊስ በጅ፣ ምንም እንኳ እጅግ ዐዋቂ የታሪክ ምሁር ቢሆኑም፣ እዚህ ላይ ተሳስተዋል።
በእርግጥ በጣም የሚያስወቅስ ስህተት አይደለም። በወቅቱ የተገኘውን መረጃ ነው የጻፉት፡፡ ከዚያ ወዲህ፣ ባለፉት መቶ ዓመታት በርካታ ጥናቶች ተካሂደዋል። ብዙ አዳዲስ መረጃዎች ተገኝተዋል።
በሥዕል ያጌጡ የሃይማኖት መጻሕፍት ጥንት ከ1500 ዓ.ም በፊትም በኢትዮጵያ ነበሩ። ይህን የሚያሳዩ ጥንታዊ ቅርሶች በምሁራ ዘንድ መጠቀስ የጀመሩት ባለፉት 60 ዓመታት ነው፡፡
አንዲት እንግሊዛዊ ተመራማሪ “የአባ ገሪማ ገዳም መነኮሳ ጥንታዊ የሃይማኖት መጻህፍት አስይተውኛል” ብለ መጻፏ ለለሎች አጥኚዎ በር ከፋች ሆኗል፡፡
የተመራማሪዋን ጥቆማ በመስማት የፈረንሳይና የእንግሊዝ ተመራማሪዎች በየፊናቸው መጥተዋል፡፡ በሥዕል ያጌጡ ጥንታዊ የሃይማኖት መጻህፍትን በፎቶና በማይክሮ ፊልም ሰንደዋል፡፡
በየበኩላቸው ባደረጉት ጥናትም፣ በሥዕል ያጌጡት የሃይማኖት መጻሕፍት በኢትዮጵያ የአንድ ሺ ዓመት ዕድሜ ሳይኖራቸው አይቀርም ሲሉ ተልጸዋል፡፡ የተመራማሪዎች ጥናት በዚህ አልተቋረጠም፡፡ የቅርሶቹን ዕድሜ በሳይንሳዊ ዘዴ በስሌት ለማረጋገጥ ናሙናዎችን ወስደው መርምረዋል፡፡
ነገር ግን፣ የምርመራዎቹ ውጤት ከጠበቁት ውጭ ስለሆነባቸው ለማመን በእጅጉ አመነቱ። እንደገና ተጨማሪ የናሙናዎች ጥናት ያካሂዱት የእንግሊዝ የኦክስፎርድ ተመራማሪዎች ናቸው፡፡ የጥናታቸው ውጤት ከቀድሞ ግምታቸው በእጅጉ የሚበልጥ ነው።
በግዕዝ የተጻፉና በሥዕል ያጌጡ የሃይማኖት መጻሕፍት በኢትዮጵያ ውስጥ ከአውሮፓ የሚቀድም ረዥም ታሪክ እንዳላቸው የተረጋገጠውም ይህን በመሰለ ረዥም የጥናት ምልልስ ነው።
በሥዕል ያጌጡ የሃይማኖት መጻሕፍት ከአውሮፓ የተኮረጁ አይደሉም። እንዲያውም፣ በአባ ገሪማ ገዳም የተገኙት በሥዕል ያጌጡ መጻሕፍት በጥንታዊነታቸው በመላው ዓለም ተወዳዳሪ የላቸውም ተብሏል።
በእርግጥ፣ እነዚህ የጥናት ግኝቶች ከመቶ ዓመት በፊት አይታወቁም ነበር። እናም ዝነኛው የእንግሊዝ ሙዝዬም የቅርሶች ዋና ኀላፊ፣ የዛሬ 95 ዓመት ባሳተሙት መጽሐፍ ላይ የተሳሳተ ሐሳብ ቢያሳትሙ አይገርምም።ዋናው ነጥብ ግን፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ሰዎች ከገመቱትና ከጠበቁት በላይ ጥንታዊ ቅርሶች መገኘታቸውና ቅርስነታቸው እያደር የሚደምቅ መሆኑ ነው።


Page 11 of 703