Administrator

Administrator

“መንግስት የእንቦጭን ጉዳይ እንደ ብሄራዊ አጀንዳ ቢይዘው ጥሩ ነው”
ዩኒቨርሲቲው ዘንድሮ 11 ቴክኖሎጂዎችን አስተዋውቋል
በአገሪቱ ግዙፍ የምርምር ማዕከል እያስገነባ ነው

ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ በተለያዩ የትምህርት ዘርፎች ያሰለጠናቸውን 6536 ተማሪዎች በመጀመሪያና በሁለተኛ ድግሪ ያስመረቀው የጎንደር ዩኒቨርሲቲ፤ችግር ፈቺ የቴክኖሎጂ ፈጠራዎች ላይ እየሰራ መሆኑን አስታውቋል፡፡ በሀገሪቱ ቀዳሚ ነው የተባለ የቴክኖሎጂ ምርምርና ፈጠራ ማዕከል ግንባታም እየተጠናቀቀ ነው ተብሏል፡፡ ዘንድሮ 11 አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ያስተዋወቀው ዩኒቨርሲቲው፤ ስድስቱን በቀጥታ
ለተጠቃሚ መሥሪያ ቤቶች አስተላልፏል፡፡ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማሩ ጎን ለጎን ፕሮጀክቶችንም ተወዳድሮ በማሸነፍ እየሰራ እንደሚገኝ
የጠቆመ ሲሆን በአማራና ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች የጤና ተቋማት የመረጃ አያያዝን ለማዘመን ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ጋር የ3.5 ሚሊዮን ዶላር ፕሮጀክት ስምምነት መፈጸሙን አመልክቷል፡፡
ጎንደር ዩኒቨርሲቲ በከተማዋ ነዋሪዎች ዘንድ የሚከበር ግዙፍ የትምህርት ተቋም መሆኑ ይታወቃል፡፡ ዩኒቨርሲቲው በማህበራዊ አገልግሎት ዘርፍ ባደረገው እንቅስቃሴ፣ ለከተማዋ ንፁህ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክት የ16 ሚሊዮን ብር ድጋፍ ያደረገ ሲሆን በነዋሪው ዘንድከፍተኛ ተወዳጅነትን ላተረፈው ፋሲል ከነማ (አፄዎቹ) የስፖርት ክለብም የ4 ሚሊዮን ብር ድጋፍ ሰጥቷል፡፡ ለከተማው ነዋሪዎች ያስገነባው ግዙፍ የሪፈራልሆስፒታልም ከዩኒቨርሲቲው ሰናይ ተግባራት መካከል የሚጠቀስ ነው፡፡
የዩኒቨርሲቲው የኢንዱስትሪና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዲፓርትመንት በበኩሉ፤ በእንቦጭ አረም ከፍተኛ የመድረቅ ስጋት የተጋረጠበትን የጣና ኃይቅን
ለመታደግ ከፍተኛ ጥረት እያደረገ መሆኑ ተገልጿል።በዩኒቨርሲቲው የቴክኖሎጂ ሽግግር ዳይሬክተርና የመካኒካል ኢንጅነሪንግ መምህር አቶ ሰለሞን መስፍን፤እንቦጭ አረምን ለመከላከል እየተደረገ ያለውን ጥረትና በአጠቃላይ በዩኒቨርሲቲው የቴክኖሎጂ ፈጠራ ዙሪያ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ተከታዩን ቃለ-ምልልስ አድርገዋል፡፡


 እንቦጭ አረምን ለማጥፋት እያደረጋችሁት ካለው ጥረት እንጀምር----
በጣና ላይ የተከሰተውን እንቦጭ አረም፣ በሰው ኃይል በእጅ ለማንሳት መሞከር የማይቻል ነው። የግዴታ ማሽን ያስፈልጋል፡፡ በቪክቶሪያ ኃይቅ ላይ ተከስቶ የነበረን እንቦጭ አረም ለማንሳት ጥቅም ላይ የዋለው ማሽን ነው፡፡ ከተንሳፋፊ ጀልባ ጋር ተገጣጥሞ የሚሰራ ማሽን ነው አረሙን ሊያነሳ የሚችለው፡፡ የጣና ኃይቅ ላይ የተከሰተውን ይህን አረም ለማንሳትም  በራሳችን ተነሳሽነት፣ በዩኒቨርሲቲው የምህንድስና ክፍል ውስጥ አንዱን ማሽን ገጣጥመን እያጠናቀቅን ነው፡፡ ለዚሁ አረም ማጥፊያነት ብቻ ነው ይህ ማሽን የተሰራው፡፡
ማሽኑ እንዴት ነው አረሙን ለማጥፋት ጥቅም ላይ የሚውለው?
ከፊት ባለው (አካፋ መሰል) አካሉ ተንሳፋፊውን አረም እየጎተተ፣ ወደ ውስጥ በመቀረጣጠፍ ያስገባዋል፡፡ መሃል ላይ ባለው የማሽኑ ክፍል ደግሞ አረሙ ይፈጫል፣ የተፈጨው ተመልሶ ውሃው ላይ አይጣልም፤ ምክንያቱም በማንኛውም ሁኔታ አረሙ በስሩም፣ በግንዱም የመራባት አቅም ስላለው፣ በቋት ተጠራቅሞ ከኃይቁ አካባቢ በራቀ ቦታ ላይ ይጣላል፡፡ በሌላው ሀገር መሰል አረምን ለማጥፋት ስራ ላይ የሚውሉ ማሽኖች፤ የተፈጨውን  አረም የማጠራቀሚያ የራሳቸው ቋት የላቸውም፡፡ ወደ ሌላ ጀልባ በመገልበጥ ነው የሚያጠራቅሙት፡፡ እኛ ግን ማሽኑ የራሱ ቋት እንዲኖረው አድርገን ነው የሰራነው፡፡
የዚህ አረም የጉዳት መጠን እንዴት ይገለጻል?
 አረሙ በባህሪው ከመሬት ጋር የሚገናኝ ስር የለውም፤ ዝም ብሎ ውሃው ላይ ነው እየተራባ የሚንሳፈፈው፡፡ በዚህ ሂደት ውሃውን እየመጠጠው በማድረቅ፣ ደረቅ መሬት እየፈጠረ ይሄዳል፡፡ በአሁን ወቅት የሃይቁን ዳርቻ ብንመለከት፣ በዚህ መንገድ አረሙ መሬት ፈጥሯል፡፡ አረሙ በባህሪው ውሃ ይወዳል፡፡ ውሃውን ደግሞ ቀድሞ ከነበረው ሦስት እጥፍ ነው የትነት መጠኑን የሚያሳድገው፡፡ ለዚያም ነው ሃይቆችን ሙሉ ለሙሉ የሚያደርቀው፡፡ ለምሳሌ ከአፍሪካ ታላላቅ ወንዞች አንዱ በሆነው ዛምቤዚ ወንዝ ላይ የተፈጠረው እንቦጭ አረም፣ የኃይል ማመንጫ ኃይሎች ሁሉ እንዲዘጉና እንዲቋረጡ አድርጓል፡፡ ለኛም የህዳሴ ግድብ ይሄ አረም ትልቅ ስጋት ነው፡፡ ምክንያቱም በቀላሉ እየተንሳፈፈ ከዚህ ወደ ግድቡ መሄድ የሚችል ነው፡፡ ወደፊት ፕሮጀክቱ ሲጀምር ፈተና ነው የሚሆንበት፡፡
አረሙ የጤና ችግርም ያመጣል፡፡ በባህር ትራንስፖርት ላይም ከፍተኛ ተፅዕኖ አለው፡፡ የዓሳ ሀብት ላይም ከፍተኛ ተፅዕኖ ያሳድራል፡፡ ዓሳዎች እንዳይራቡ ያደርጋል፡፡ የኦክስጅን ዝውውሩን ስለሚገታ መራባት አይችሉም፡፡ ለዓሣ አጥማጆችም ፈተና ነው የሚሆንባቸው፤ መረባቸውን መዘርጋት አይችሉም፡፡
አረሙ ከስሩ ሊጠፋ የሚችለው ምን ቢደረግ ነው?
አረሙን ማጥፋት አይቻልም፤ እንዳይስፋፋ ማድረግ ነው የሚቻለው፡፡ እኛ በሰራናቸው ማሽኖች ነው አረሙን መግታት የሚቻለው፡፡ እኛ የሰራነው አንድ ማሽን ነው፤ ነገር ግን አሁን በጎንደር አዋሳኝ ብቻ የተከሰተውን አረም ለማስወገድ ተመሳሳይ ስድስትና ሰባት ያህል ማሽኖች ያስፈልጋሉ። ምናልባት በባይሎጂካል መንገድ አረሙን የሚመገቡ ጢንዚዛዎችን በማምጣት በረዥም ጊዜ መስፋፋቱን መቀነስ ይቻል ይሆናል፤ ግን ይሄ ጊዜ ይወስዳል፡፡ የኛ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪ ዶ/ር ሳሙኤልም በፈንገስ አረሙን መቋቋም የሚችል ንጥረ ነገር ለማዘጋጀት ሞክሯል፡፡ እነዚህ ምርምሮች በላብራቶሪ ሙከራ ደረጃ ውጤታማ ናቸው፡፡ ነገር ግን በመስክ ላይ በሚገባ መሞከር ያስፈልጋል። ሌሎች ሀገሮች ኬሚካልም ይጠቀማሉ፡፡ የኛ ግን ሃይቅ እንደመሆኑም ብዝሃ ህይወትን ስለሚጎዳ ኬሚካል መጠቀም አይቻልም፡፡
ግን አረሙ ከየት ነው የመጣው?
 አመጣጡ ላይ ይህ ነው ተብሎ የሚጠቀስ ምክንያት እስካሁን አልቀረበም፡፡ መጀመሪያ የታየው መገጭ ወንዝ ላይ ነው፡፡ ግን ወደ ሀገር ውስጥ እንዴት እንደመጣ አይታወቅም፡፡ በእርግጥ ከኛ ቀድሞ በምስራቅ አፍሪካ ሀገራት፣ በተለይ በቪክቶሪያ ሃይቅ ባለቤት ሀገሮች ነው የገባው፡፡ ግን ወደኛ ሀገር እንዴት እንደመጣ አይታወቅም፡፡ አንዳንዴ ከከተማ የሚመጡ ፍሳሾች እንዲህ አይነቱን አረም የመፍጠር እድል አላቸው፡፡ ከጎንደርም ሆነ ከሌሎች ከተሞች የሚለቀቁ ፍሳሾች ከጣና ሃይቅ ጋር መገናኘት የለባቸውም፡፡ ግን መነሻው ይሄ ፍሳሽ ነው ማለት አይቻልም፡፡ ጥናትና ምርምሮች መካሄድ አለባቸው። በዋናነት የአረሙ መነሻ ደቡብ አሜሪካ ነው፡፡ አረሙ አበባ ያወጣል፡፡ በደቡብ አሜሪካ ይሄን አበባ ለቤት ማስዋቢያና ጌጣጌጥ ይጠቀሙበት ነበር። አሁን ይሄ አረም በዓለም ላይ ካሉ አስር አስከፊ አረሞች አንዱ ነው፡፡
በጣና ላይ የተከሰተው አረም በፈረንጆቹ 2014/15፣ 44 ሺህ ሄክታር መሸፈኑን የሚያመለክት መረጃ አለኝ፡፡ አረሙ ደግሞ ከ12 እስከ 18 ቀናት ውስጥ ራሱን በእጥፍ የማባዛት ባህሪ አለው፡፡ ይሄ በጣም አደገኛ ባህሪው ነው፡፡ እኛ ሀገርም ሆነ ሌሎች ሀገሮች ላይ ይሄ አረም ሃይቆችን አድርቋል። ጣና ላይም ይሄ የማይደገምበት ምንም ምክንያት የለም። ይሄን ጉዳይ ቢቻል መንግስት እንደ ብሔራዊ አጀንዳ ቢይዘው ጥሩ ነው፡፡ ዩኒቨርሲቲውና ጥቂት የመንግስት አካላት ብቻቸውን ሊወጡት አይችሉም። ሌላ የከፋ ችግር ከመፈጠሩ በፊት ሊታሰብበት ይገባል፡፡ ይሄን ጉዳይ የሚከታተል አካል በመንግስት ተቋቁሞ ቢሠራ መልካም ነው፡፡
የሰራችሁት ማሽን ምን ያህል አረም በቀን ያፀዳል?
 በሰዓት እስከ 5 ቶን ማስወገድ የሚችል ነው። አረሙ ውሃ የመያዝ አቅሙ ከፍተኛ ነው፡፡ ማሽኑ ውሃውን እየጨመቀ ነው የሚፈጨው፡፡ ይሄን ማሽን የሚያንቀሳቅሱ ባለሙያዎችም አሉን፡፡ ሐምሌ መጨረሻ ላይ ማሽኑ ወደ ሀይቁ ተወስዶ ይሞከራል፡፡ ወደ ስራም ይገባል፡፡ ተጨማሪ ማሽን ይመረት ከተባለም ጨምረን እናመርታለን፡፡ አረሙን ለማጥፋት በሰው ኃይል ቢሞከር ውጤቱ እምብዛም ነው፡፡ አወጋገዱም አስተማማኝ አይደለም፡፡ አረሙ መልሶ ችግር እንዳይፈጥር በአግባቡ መወገድ አለበት፡፡
ታዲያ የተፈጨው አረም ሲጣል መልሶ ችግር አይፈጥርም?
የተለያዩ ሀገሮች ይሄን አረም ከሀይቁ ወይም ከውሃ አካሉ ካስወገዱት በኋላ ለተለያየ ነገር ይጠቀሙበታል፡፡ ከአረሙ ባዮጋዝ፣ ሜቴን ጋዝ ማግኘት ይቻላል፡፡ ከአረሙ ከሰልን ተክቶ ሊነድ የሚችል ብሪኬት መስራት ይቻላል፡፡ ኬንያዎች በቅርቡ ለዱባይ ማዳበሪያ ፋብሪካ ኤክስፖርት አድርገዋል፡፡ ለማዳበሪያ ምርት ይሆናል፡፡ ኬንያዎች ከኩባንያው ጋር ውል ገብተው፣ እየፈጩ ኤክስፖርት በማድረግ ገቢ እያገኙበት ነው፡፡ ቡና እና ሻይ ኤክስፖርት አድርገው ካገኙት ገቢ በላይ ከዚህ አረም አግኝተዋል፡፡ ለዚህ ነው መንግስት በዚህ ጉዳይ ጣልቃ መግባት አለበት የምለው፡፡ በቅርቡ አስራ አንድ ሚሊዮን ኩንታል ማዳበሪያ ነው ከውጭ ያስገባነው፡፡ ይሄን ከሸጠልን ኩባንያ ጋር ለምን አረሙን ለመሸጥ አንዋዋልም? ይሄን መንግስት ማሰብ አለበት፡፡ ትልቁ ነገር ይሄን አረም ማስወገድ ቢሆንም የተወገደውን በዚህ መልኩ ለሀገር ጥቅም ማዋል ይቻላል፡፡
ዩኒቨርሲቲው በአዳዲስ ቴክኖሎጂ ምርምሮችና ፈጠራዎች ላይ እየተሳተፈ ነው ተብሏል፡፡ ስለዚህ ጉዳይ ሊያብራሩልኝ ይችላሉ?
በዚህ ዓመት ብቻ ወደ 38 የሚደርሱ የቴክኖሎጂ ሽግግሮች ተመርተዋል፡፡ ከነዚህ ውስጥ አዳዲስ ፈጠራዎችም አሉን፡፡ እነዚህ ቴክኖሎጂዎች እኛ ጋር መቅረት የለባቸውም፤ ስራ ላይ መዋል አለባቸው የሚል እቅድ ይዘን ወደተጠቃሚዎችም እያደረስን ነው፡፡ በቅርቡ አራት የቴክኖሎጂ ፈጠራዎችን ወደ ተጠቃሚዎች አድርሰናል፡፡ ለምሳሌ በቱሪዝም ጉዳይ የጀርመንና የአማርኛ ቋንቋ መተግበሪያ (Application) ሰርተናል፡፡ በተለይ ለአስጎብኚዎች ይሄ መተግበሪያ በእጅጉ ይጠቅማል፡፡ በአንድሮይድ ስልኮች ላይ በቀላሉ የሚጫን፤ ጀርመንኛን ወደ አማርኛ፣ አማርኛን ወደ ጀርመንኛ ቋንቋ የሚቀይር መተግበሪያ ነው፡፡ ቴክኖሎጂውን ለአስጎብኚዎች፣ ለዞኑ ቱሪዝም መምሪያ አስረክበናል፡፡ ሌላው የሰሜን ጎንደርና የደቡብ ጎንደርን የጉብኝት ቦታዎችና አንዳንድ ሆቴሎችን መገኛ የያዘ ዲጂታል ካርታ አዘጋጅተን አስረክበናል፡፡ ይህ ካርታ በህትመትም ይገኛል፡፡
የጎንደር፣ ላሊበላና አክሱምን የሚያገናኝ ካርታም በኛ የጂአይኤስ ባለሙያዎች ተሰርቷል፡፡ ይሄ የቱሪዝም ኢንዱስትሪውን ከማስተዋወቅ አንፃር ጥቅሙ ከፍተኛ ነው፡፡ በተመሳሳይ በጎንደር ከተማ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ቱሪስቶች፤ ያለ ሰው እርዳታ ህንፃዎችን፣ ቤቶችን፣ ሆቴሎችን በአጠቃላይ የሚፈልጓቸውን ቦታዎች በቀላሉ ማግኘት የሚያስችላቸው የአሰሳ (Navigation) መተግበሪያ፣ የኛ ተማሪዎች ሰርተው ለጎንደር ከተማ አስተዳደር አስረክበናል፡፡
በፀሐይ ኃይል ብቻ የሚሰሩ ባለ ሦስት እግር ተሽከርካሪዎችንም ሰርተናል፡፡ በባዮ ጋዝና በሜቴን የሚነዳ መኪና ሰርተናል፡፡ ባለ ሶስት እግር ተሽከርካሪዎቹ አሁን ሙከራቸው ተጠናቆ፣በኩባንያ ደረጃ መመረት ነው የሚቀራቸው፡፡ የሚያመርቱ ኩባንያዎች መፈጠር አለባቸው፡፡ እነዚህ ከመጡ እኛ ቴክኖሎጂውን ለማካፈል  ዝግጁ ነን፡፡ እኛም ራሳችን ይሄን የሚያመርት ኩባንያ መፍጠር አለብን፡፡ ሌላኛው ለተጠቃሚዎች ያደረስነው ቴክኖሎጂያችን፣ የላፕቶፕ ባትሪን የተመለከተ ነው። ብዙ ጊዜ የላፕቶፕ ባትሪ ውድ ከመሆኑም በላይ ሲያረጅ ያለው አማራጭ መጣል ብቻ ነው፡፡ እኛ ግን አያገለግልም የተባለውን ባትሪ በቀላሉ እየሞላን ወደ አገልግሎት መመለስ የሚያስችል ቴክኖሎጂ ነው የፈጠርነው፡፡ ለወደፊት እዚሁ ማምረት የሚቻልበት ሁኔታም እየተሰራ ነው፡፡ በዚህ ቴክኖሎጂ ዘንድሮ የ106 የዩኒቨርሲቲው መምህራንን ላፕቶፖች ባትሪ ሞልተናል፡፡ የዚህ ፈጠራ ባለቤት ዩኒቨርሲቲውና የሰሩት ግለሰቦች ናቸው፡፡
ቴክኖሎጂውን ከዩኒቨርሲቲ ውጪ ላሉ ተጠቃሚዎች እንዴት ልታደርሱ አስባችኋል?
 ለህብረተሰቡ ማድረስ ጀምረናል፡፡ በጎንደር ከተማ የሚገኙ 20 ሥራ አጥ ወጣቶችንና ከዞኑም ወደ 28 ሥራ አጥ ወጣቶች፣ በድምሩ 48 ሥራ አጥ ወጣቶችን አሰልጥነን ወደ ስራ እንዲገቡ አድርገናል። ጎንደር ከተማ ላይ በዚህ ቴክኖሎጂ በመጠቀም፣ ያረጁ የላፕቶፕ ባትሪዎችን የሚሞሉ ወጣቶች አሉ። አንድ ባትሪ ከ1400 ብር በላይ ነው የሚሸጠው፡፡ ወጣቶቹ ግን በ500 ብር ነባሩን አዲስ አድርገው፣ ደንበኛው መልሶ እንዲጠቀምበት እያደረጉ ነው፡፡
ከዚህ ውጪ ለኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ብቻ ይውላል ተብሎ የሚታሰበውን የንፋስ ሀይል፣ ለከርሰ ምድር ውሃ ማውጫነት የሚያውል ቴክኖሎጂ አዘጋጅተናል፡፡ ሰሜን ደባርቅና ዳባት አካባቢ ከፍተኛ የንፋስ ፍጥነት አለ፡፡ አምባጊዮርጊስ አካባቢ በንፋስ ኃይል የሚሰራና 120 ሜትር ጥልቀት ውስጥ ያለን ውሃ ወደ ገፀ ምድር የሚያፈስ ፓምፕ ሰርተናል፡፡ እሱን በቅርቡ እናስመርቃለን፡፡ ይህ ከከርሰ ምድር የወጣ ውሃ ንፁህ ስለሆነ ለመጠጥም ይሆናል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ሰው ሰራሽ ሃይቅ ለመፍጠሪያነት ይውላል፡፡
እኛም ለመስኖ ልማት የሚውል ሃይቅ ለመፍጠር አቅደን፣ ገበሬዎች የሚበዙበትን አካባቢ መርጠን ነው ፓምፑን የተከልነው፡፡ ውሃውን ለመስኖ እንዲጠቀሙ አቅደን ነው ይሄን ያደረግነው። ሁሉንም መጥቀስ ጊዜ ይወስዳል እንጂ እንደዚህ ያሉ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ችግር ፈቺ 38 የቴክኖሎጂ ሽግግሮችና ፈጠራዎችን አዘጋጅተናል፡፡
የ3D ማተሚያ ማሽን፣ ዶክመንቶችን የማጠራቀሚያ አፕሊኬሽን፣ የፍ/ቤት ጉዳዮችን መከታተያ መተግበሪያ አፕሊኬሽን ሰርተናል፡፡ የፍ/ቤት መከታተያ መተግበሪያው በተለይ የሀገራችንን የፍ/ቤት አሰራር ለማዘመን እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ ባለጉዳዮች በቀጥታ ቀጠሮአቸውን እንዲከታተሉ ከማድረጉም ባሻገር በአንድ ጉዳይ ላይ ዳኞች ቢለዋወጡ እንኳ ቀጣዩ ዳኛ የቀድሞው ከቆመበት እንዲቀጥል በቀላሉ መረጃ የሚሰጠው ይሆናል፡፡
ከግብርና ጋር በተያያዘ ምርታማ ዘሮችን የማላመድ፣ ወተትን ከቅቤ በቀላሉ የሚለይ ማሽንም ሰርተናል፡፡ በቅርቡ ከተጠቃሚዎች ጋር ርክክብ እናደርጋለን፡፡ እስከ ሐምሌ 30 ሁሉም የተጠናቀቁ የምርምር ስራዎቻችንን ለተጠቃሚዎች የማድረስ እቅድ ነው የያዝነው፡፡ ለ2010 ደግሞ ሌሎች እቅዶች ይዘናል፡፡ ፓተንት ያገኘንባቸውን ቴክኖሎጂዎች በርካታ ኩባንያዎች  እንድንሸጥላቸው እየጠየቁን ነው፡፡ ለወደፊት በተገቢው መንገድ እንዲያገኙት ይደረጋል፡፡
አሁን የቴክኖሎጂ ፈጠራ ማዕከላችሁ አነስተኛ ነው፡፡ ለወደፊት ምን ታስቧል?
ኢትዮጵያ ውስጥ ካሉ ዩኒቨርሲቲዎች ግዙፍ የሚባለውን የወርክሾፕና የፈጠራ ማዕከል እየገነባን ነው፡፡ ግንባታውም በመጠናቀቅ ላይ ነው፡፡ በርካታ የምርምር ማዕከሎችን የያዘ ግዙፍ የምርምር ማዕከል ነው፡፡ በሀገራችን የእንስሳት ህክምና ሆስፒታል የለም፡፡ ዩኒቨርሲቲው ግን ይሄን እውን ለማድረግ የእንስሳት ህክምና ሆስፒታልም እየገነባ ነው፡፡    



ቀን አንዲት ድመት አንድ አውራ ዶሮ ታይና አድፍጣ ልትበላው ትፈልጋለች፤ በእርግጥ ልትበላው አይገባትም በህጉ፡፡ አውራ ዶሮው በመሠረቱ፤ ድመት አውራ ዶሮ የመብላት ባህል የላትም በሚል በቸልተኝነት ግቢው ውስጥ እየተጐማለለ ይዝናናል፡፡ አመሻሽ ላይ ነው፡፡
በመጨረሻ ድመቷ ዘልላ ከመያዙዋ በፊት፤ ምክንያት እንደሚያስፈልጋት አሰበችና እንዲህ አለችው፤
“እንደምን ውለሃል አያ አውራ ዶሮ?”
አውራዶሮም፤ “ደህና ነኝ፡፡
እንደምን ውለሻል እመት ድመት”
እመት ድመትም፣
“ሌሊት ሌሊት እየጮህክ ሰዎችን ከእንቅልፋቸው እየቀሰቀስክ እስከ ዛሬ ስትረብሽ ከርመሃል፡፡ ከእንግዲህ ግን ይሄ አጉል የምትጮኸው ነገር ያበቃል፡፡ አሁን እርምጃ ልወስድብህ ነው” አለችው፡፡
አውራ ዶሮው፤ እመት ድመት እንደተሳሳተች በመገመት፤
“እመት ድመት ሆይ በጣም ተሳስተሻል፡፡ እኔ የምጮኸው ሰዎች ማለዳ እንዲነሱና እንዲነቁ፣ የዕለት ሥራቸውን በጠዋት እንዲጀምሩ፤ በዚህም ኑሯቸውን ለማስተካከል እንዲችሉ እንጂ ለመረበሽ አይደለም፡፡ እንዲያውም እኔ ባልኖር በትክክል ጊዜን ለማወቅ አይችሉም ነበር” አለና ተከላከለ፡፡
እመት ድመት ግን በግትርነት፤
“ሰዎች ጊዜውን ለማወቅ ቻሉም አልቻሉም፣ እኔ እራቴን ሳልበላ ማደር የለብኝም” ብላ ዘላ ቀጨም አደረገችው፡፡
* * *
የማናቸውም ጥሩ ምክንያት መኖር አንዴ በልቡ ለመብላት ያሰበን ሰው ከማድረግ አያግደውም፡፡
“ሊበሏት ያሰቧትን አሞራ ጅግራ ይሏታል” የተባለው ተረት የተገላቢጦሽ ሆነ ማለት ነው፡፡
ህዝብን ተሳታፊ የማያደርግ እንቅስቃሴ ዘላቂ አይሆንም፡፡ አመራር ሁሉ ሀቀኛ ተመሪ ያገኝ ዘንድ ግድ ነው፡፡
ተሳታፊነት በውዴታ እንጂ በግዴታ የሚሆን አይደለም፡፡ የህዝብ ቀዳሚ አብሪ ወጣቱ ነው፡፡ ወጣቱን ያልያዘ (መያዝም ቢሉ በውዴታና ከልብ) ለውጥ የሚያቆጠቁጥ አይሆንም፡፡ ቻይናዎች “ጀልባ ማንቀሳቀስ ከፈለግህ ወደ ወንዙ መቅረብ አለብህ” የሚሉት በአግባቡ ለመቅዘፍ እንዴት እንደሚቻል ልብ እንድንል ነው፡፡
መሪና ተመሪ ልባዊ ግንኙነት ሊኖራቸው ይገባል፡፡ መሪና ተመሪ የአዕምሮ አቅም መመጣጠን (Congruence of wavelength) ሊኖራቸው ይገባል፡፡ መሪና ተመሪ የአቋም መጣጣም ሊኖራቸው ይገባል፡፡ መሪና ተመሪ ከጌታና ሎሌ ግንኙነት የተላቀቁ መሆን አለባቸው፡፡ መሪና ተመሪ የመተካካት ባህል ሊኖራቸው ይገባል እንጂ አይተኬ - ነኝ (indispensable) የሚል ሰው የሚኖርበት መሆን የለበትም፡፡
በተለይም ተመሪው ወይም ተከታዩ “መሪዬ ከሌለ ወዴት እደርሳለሁ?” የሚል ሥጋት ያለው ከሆነ፤ አንድም መሪው ብቸኛና አይተኬ ነኝ እንዲል ይገፋፋዋል፤ አንድም ደሞ ተመሪው ራሱን ለተተኪነት እንዲያዘጋጅ፤ በቆመበትና ባለበት ሁኔታ ያግተዋል፡፡ ቻይናዎች እንደሚሉት “ከዶሮዎች መካከል ያለች ፒኮክ በቀላሉ ትለያለች” ማለት ነው፡፡
መሪው አይተኬ ሆነ ማለት ይኼው ነው፡፡ ማንኛውም የፖለቲካ መሪ አይተኬ ነኝ ብሎ ሲያስብ ብዙ ዓይነት ባህሪያትን ያንፀባርቃል፡እኔ ያልኩት ምንጊዜም ልክ ነው ከሚል ተነስቶ፤ እኔ ያልኩት ካልተፈፀመ ሞቼ እገኛለሁ፤ ይላል፡፡ ያጠናውን፣ የፃፈውን የተናገረውን በሀገሩ ላይ ይፈትናል፡፡ ወይም ይፈትሻል፡፡ ኢኮኖሚው በእጁ ይወድቃል፡፡ በየጉዳዩ ላይ ቅድመ ፍርድ ይሰጣል፡፡ “ስታሊን እንደንስ” ሲል ማን ቁጭ ብሎ ያያል” ይላል ክሩስቼቭ። እሱ ሲስቅ አገር ይስቅ ዘንድ፣ እሱ ሲቆጣ አገር ይቆጣ ዘንድ ግድ ይሆናል ማለት ነው፡፡
አሁን አሁን የእኛን ሙሰኞች ከሙስና እንዲፀዱ ማድረግ “ውሻን አይጥ መያዝ ማስተማር” ዓይነት ከባድ ነገር እየሆነ መጥቷል፡፡ ሌባ ያዝ ተብሎ የተላከው፤ ራሱ ሲሰርቅ ይገኛል፡፡ ሲሰርቅ ተይዞ እሥር ቤት የገባው፤ ሌላ ዓይነት ሌብነት ተምሮ ይወጣል “ሞኝ ያስራል ብልጥ ይማራል” የተባለው ዓይነት፡፡
የሙስና ዲግሪ የሚሰጥ ቢሆን፤ በመሬት፣ በቤት፣ በቢሮክራሲ፣ በቴክኖክራሲ፣ በሌበር - አሪስቶክራሲ፣ በብሔር - አሪስቶክራሲ የሚሸለሙ ስንቶችን አፍርተን ነበር - ባይልልን ነው እንጂ፡፡
“የመጨረሻው ድህነት በህይወት ውስጥ ምንም ምርጫ ማጣት ነው፡፡”ይሉናል፤ የፈረንጅ ፀሐፍት፡፡ ወይም ፀጋዬ ገ/መድህን እንደሚለን፤ “ማጣት፤ በነብስህ ጫፍ ሩቅ አልመህ ሁሉን መሳት” ማለት ነው፡፡
በየጉዳዩ ላይ ምርጫ ያጣ ህዝብ እጅግ ደሀ ህዝብ ነው፡፡ ስለ ዲሞክራሲ፣ ስለ ፍትህ፣ ስለ ገዛ ኢኮኖሚው፣ ስለ መናገር ነፃነቱ፣ ስለ ቤት ንብረቱ አማራጭ የሌለው፤ የዓለም ባንክ ባልደነገገው መንገድ የድህነት ምርኮኛ ነው፡፡ ከዚህ ይሰውረን፡፡ በየአቅጣጫው ዙሪያ ገባውን በችግር ማጥ የተወረረ ህዝብ ያልታደለ ነው፡፡ ያም ሆኖ እንደ መኮንኑና እንደ ጄኔራሉ ውይይት፤ የታሪክ ምፀት ባለቤት መሆኑ ባይቆጭ ያንገበግባል፡፡
መኮንኑ - “ኧረ ዙሪያውን ተከበናል፤ ጄኔራል?” ሲል
ጄኔራሉ - “አሪፍ ነዋ በፈለግነው አቅጣጫ እንተኩሳለን” አለ አሉ፡፡
አዎንታዊነት? ጨለምተኝነት? ትራጆ - ኮሜዲ? ወይስ ፋርስ? ዞሮ ዞሮ ምፀት ነው፡፡

አሐዱ ኤፍኤም 94.3 ሬዲዮ ጣቢያ የሙከራ ስርጭቱን የጀመረ ሲሆን ከሐምሌ 15 ቀን 2009 በኋላ መደበኛ ፕሮግራሞቹን እንደሚጀምር አስታወቀ፡፡
ጣቢያው በይፋ ስርጭት መጀመሩን አስመልክቶ የሬዲዮ ጣቢያው የሥራ ኃላፊዎች ሰሞኑን  ባዘጋጁት ጋዜጣዊ መግለጫና የጉብኝት ፕሮግራም ላይ እንደተናገሩት፤ከስምንት ዓመታት አድካሚና እልህ አስጨራሽ ሥራ በኋላ ጣቢያው የብሮድካስቲንግ ፈቃድ አግኝቶ ተቋቁሟል፡፡  
የኤዲስቴይለር ትሬዲንግ እህት ኩባንያ በሆነው ኤዲስቴይለር ሚዲያ ሴንተር ውስጥ የተቋቋመው ይኸው የሬዲዮ ጣቢያ፤የኢትዮጵያውያን ድምፅ በመሆን ኢትዮጵያዊ እሴቶችን ለማስታወስና ለማስተዋወቅ እንዲሁም ማህበራዊና ባህላዊ ህይወትን ለማጠናከር እንደሚሰራም ኃላፊዎቹ አስታውቀዋል፡፡  
የኤዲስቴይለር ትሬዲንግ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ እሸቱ በላይ በመክፈቻ ፕሮግራሙ ላይ እንደተናገሩት፤ ጣቢያው እንደ ስሙ በመረጃ፣ በቴክኖሎጂና በአቀራረቡ ቀዳሚ ሆኖ አድማጮቹን ቀዳሚ ለማድረግ ይተጋል፡፡ በአዳዲስ የቴክኖሎጂ መሳሪያዎችና ብቃት ባላቸው ባለሙያዎች በማደራጀትም የተቋቋመበትን ዓላማ ከግብ ለማድረስ ይሰራል፡፡ ጣቢያው በሚዲያው ዘርፍ የልዕቀት ማዕከል (Center of Excellence) የመሆን ራዕይ እንዳለውም ሥራ አስፈጻሚው ተናግረዋል፡፡
የሬዲዮ ጣቢያው ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ጥበቡ በለጠ በበኩላቸው፤የሬዲዮ ጣቢያው በአገሪቱ የሚገኙትን የኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያዎች ቁጥር በአንድ ከፍ ከማድረግ በዘለለ የራሱን ቀለምና መልክ ይዞ በማህበረሰቡ አኗኗርና አስተሳሰብ ላይ አዎንታዊ ለውጥ ለማምጣት ይሰራል ብለዋል፡፡
የአሐዱ ሬዲዮ ዋና አዘጋጅ አቶ ካሣ አያሌው ካሳ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት፤ጣቢያው በረቀቁ የቴክኖሎጂ መሳሪያዎችና በዘመናዊ ስቱዲዮ የተደራጀ ከመሆንም ባለፈ በሙያው ልምድ ባካበቱና ለሙያቸውና ለሚያገለግሉት ህዝብ ክብር ባላቸው ሙያተኞች የተደራጀ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም፤ ጋዜጠኛው ራሱ የቴክኒኩንም ሥራ እየተቆጣጠረ ፕሮግራሞችን የሚሰራበት አዲስ አሰራር ተግባራዊ እንደሚደረግም ገልፀዋል፡፡
ጣቢያው ከሬዲዮ ስርጭቱ በተጨማሪ የድረ ገፅ መገናኛ ብዙኃን እያደራጀ እንደሚገኝና ድረ ገፁ የአሐዱ ሬዲዮንን መሰረታዊ ባህርያት ተከትሎ፣ ከድምፅ ባሻገር መረጃዎችን በፅሁፍ፣ በፎቶና በቪዲዮ አስደግፎ እንደሚያቀርብና የሬዲዮ ስርጭቱንም በኢንተርኔት በቀጥታ እንደሚያስተላልፍ ተነግሯል፡፡
በአሁኑ ወቅት በሙከራ ስርጭት ላይ የሚገኘው የሬዲዮ ጣቢያ፤ከመጪው ሐምሌ 15 ቀን 2009 ዓ.ም ጀምሮ መደበኛ ስርጭቱን እንደሚጀምርም ተገልጿል፡፡



ወጋገን ባንክ ባለፉት 20 ዓመታት ሲጠቀምበት የነበረውን ዓርማ በአዲስ ቀየረ፡፡ ዓርማው የባንኩን ዋነኛ እሴቶችና በ2025 በአፍሪካ ከሚገኙ 10 ስመ ጥርና ተፎካካሪ ባንኮች አንዱ ለመሆን የነደፈውን ራዕይ የሚያንፀባርቅ እንደሆነ ተገልጿል፡፡
ባንኩ፤ ከትናንት በስቲያ በሸራተን ሆቴል አዲሱን ዓርማ ባስተዋወቀበት ሥነ-ሥርዓት ላይ የባንኩ የዲሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ተፈሪ ዘውዱ፣ አዲሱ የንግድ ምልክትና ዓርማ፣ ያለፉትን ዓመታት ስኬት የወደፊቱን ብሩህ ተስፋና የደረስንበትን ጥሩ መሠረት እንዲያንፀባርቅ እንዲሁም የመጪውን ትውልድ ስሜትና ዝንባሌ ከግምት ውስጥ በማስገባት ጭምር የተቀረጸ ነው ብለዋል፡፡
አዲሱ አርማ ወጋገን ባንክ በ20 ዓመታት ቆይታው ለደንበኞቹ ከሰጠው አገልግሎት ያበረከታቸውን መልካም እሴቶችና ልምዶን ጠብቆ ለማቆየት፣ የባንኩን አገልግሎት ተጠቃሚዎች ፍላጎት ለማርካት የተዘጋጀ ብራንድ መሆኑን ጠቅሰው፣ ዓርማው ላለፉት 12 ወራት ሲዘጋጅ ቆይቶ መቆየቱንና ከቀረቡት አማራጮች ተመርጦ መዘጋጀቱን ገልፀዋል፡፡
የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ አርአያ ገ/እግዚአብሔር አዲሱ የባንኩ መገለጫ ዓርማ ለደንበኞችና ለሌሎች ባለድርሻ አካላት የባንኩን ራዕይ፣ ተልዕኮ፣ ዕሴቶች፣ ያለፈውን ስኬትና የወደፊት ግቡን በመወከል ከሌሎች ተወዳዳሪ ባንኮች በቀላሉ ለይተው እንዲያውቁትና እንዲያሳተዋውቁት ያደርጋል፤ የባንኩ ገጽታ በወጥነትና በትኩረት ለመሳብ የሚደረገውን ጥረት ይደግፋል ብለዋል፡፡  ውስብስብነት የሌለው፤ ሰዎች ያለምንም ችግር በቀላሉ እንዲለዩት ተደርጎ የተሰራው አዲሱ ዓርማ፣ ወጋገን ከሚለው የአማርኛ አጠራር ‹‹ወ›› እና ከእንግሊዝኛው ‹‹W›› ፊደላት የመጀመሪያዎቹን ቃላት በመውሰድ የተፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የወጋገን ባንክ አርማ ዋነኛ ቀለም ብርቱካናማ ሲሆን ጎህ ሲቀድ በሰማይ አድማስ ላይ ከሚታየው የጠዋት ፀሐይ ደማቅ ብርሃን የተቀዳ፤ በተስፋና በመልካም ምኞት የተሞላ ብሩህ ጊዜን እንደሚያመለክት ተገልጿል፡፡

የመመረቂያ ቀናችን እየቀረበ ነው ….አንዱ ቀን አልፎ ሌላው በተተካ ቁጥር ጥቁር የምንለብስበት ቀን ወደ እኛ እየቀረበ ነው፡፡ ኃላፊነት …. ቤተሰብ …. ትዳር …. ሥራ…. ወዘተ የሚባሉ ነገሮች እኛነታችንን እየጠበቁን ይገኛሉ፡፡
ተኝተን በተነሳን ቁጥር መቶ ሃያ ቀን ቀረን …. መቶ ቀን ቀረን …. ስልሳ ቀን ቀረን …. እያልን ነው፡፡ ጊዜ እየተፍገመገመ ወደ እኛ እየቀረበ ነው …. ሰቀቀን ሊገድለን ነው …. ሙሾ ሊከበን ነው …. በጥቁር ልብስ ውስጥ ልንሞሸር ነው…. መመረቃችን ለኛ ሞት ነው…. ለዛም ነው የምናለቅሰው፤ ለዛም ነው ሆዳችንን ባር ባር የሚለው፤ ለዛም ነው ጥቁር የምንለብሰው….
እንዴት ባር ባር አይለንም ….እንዴትስ ውስጣችን አይጠቁር …. እንዴትስ የእንባዎች ጅረት በጉንጫችን አይውረድ…. አዎን ያቺ የመመረቂያ ቀናችን የምትቀማን በወጣትነት ዘመናችን ያፈራናቸውን…. ጓደኞቻችንን  ነው፡፡ የዋሆቹን …. ፖለቲከኞቹን …. ቸካዮቹን …. ዘረኞቹን ….ነጭናጫዎቹን …. አፍቃሪዎቹን …. ስፖርት ወዳጆቹን ….ዘናጮቹን…….ወዘተ ነው የምትቀማን፡፡ ያቺ ቀን በደግም በክፉም ከምናውቃቸው መምህራኖችና የአስተዳደር አካላት ጋር የምትለየን ቀን ነች፡፡
ጥቁር ለመልበሳችን ብዙ አመክንዮ አለን። አዎን ከፍቶን ተምረናል …. ለቤተሰቦቻችን ብቻ ስንል ውስጣችን የማይቀበለውን የሽንፈት ታሪክ እያስተናገድንም ቢሆን ተምረናል …. ዕሳቤያችን ሁሉ ተዛብቷል …. የት ይደርሳል የተባለ ዛፍ ሆኖብናል ነገሩ …. ዓለሙ… መንደሩ…. ሁሉ ነገር ተምታቶብን ተምረናል …. ሀዘን ክንዳችንን አዝሎታል …. ሞትን ወደ ቤታችን ግባ ብለን ጋብዘነዋል …. የሚረዱንን ደጋፊዎቻችንን….. ወላጆቻችንን ሳንደርስላቸው ….  ቀና ሳናደርጋቸው በጊዜ ርዝማኔ ተነጥቀናል …. ትምህርት ዋጋ አስከፍሎናል …. የመኖር እንቆቅልሽ አልገባ ብሎናል፤ ስንትና ስንት ቀናትን ዶርማችን ውስጥ ተሸሸገን አልቅሰናል …. የምንገባበት ቢጠፋን ጊዜ ተጨንቀናል ….የተጫሩት ወንድሞቻችን ዩኒቨርስቲያችን በሚገኝበት ከተማ ውስጥ በሚገኙ ሆቴሎች በራፍ ላይ ሲባዝኑ ስናይ ውስጣችን ደምቷል …. ፈተና ቢከብደን ጊዜ በረኪና ጠጥተናል …. ኽረ እኛ ያላሳለፍነው ከቶ ምን አለ?
ታዲያ  ያለፈው ማንነታችንን የሚገልፀው ነጭ ሳይሆን ጥቁር ነው …. አዎን ጥቁር ነው መልበስ ያለብን …. በጥቁር ነው መሸፈን ያለብን …. ጥቁርማ የውስጣችን ገላጭ ነው ….ቆመን መሄዳችን …. መሳቅ መጫወታችን ….ተኝተን መነሳታችን …. እኛነታችንን አይገልጹትም …. እኛነታችንን የሚገልጸው ያ ጥቁር ልብስ ነው፡፡
ይገርማል ዩኒቨርስቲዉ ውስጥ በቆየንባቸው ዓመታት የተፈራረቁት ብርሃንና ጨለማ ስለ እኛ ምን ይናገራሉ…. ስለ እኛ ምን ያወራሉ …. ሺ ጊዜ ወድቀናል …. ሺ ጊዜ ተነስተናል …. መውደቃችን …. መሸነፋችን …. ከተራራ በላይ ገዝፎ ተነግሯል …. የተስፋ ታንኳችን በወጀብ ተመታ …. በማዕበል ተገፍታ …. ተንቃቅታ …. ተንቃቅታ….በግማሽ ጎኗ ሰምጣለች …. ሕይወታችን እዛው ከታንኳ ጋር  አብሮ ሰምጧል…. ክረምት ወደ ቤታችን ለመሄድ አስበን የትራንስፖርት ቸግሮን፣ ከቤተሰቦቻችን ጋር ሳንተያይ አንዱ በጋ አልፎ በአንዱ ላይ ተተክቶ አምስት አመት ተቆጥሯል ….የልጅነታችን ወዝ ተንጠፍጥፎ ደርቆብናል …. ገላችን  ከስሟል … ውበታችን ረግፏል …. የምንሆነውን ሳይሆን የማንሆነውን  ሆነናል …. ለተደራቢው ጥቁር ልብስ ቀሚሳችንን ጥለን …. ሱሪ ታጥቀናል …. ሱሪ መታጠቃችንን የተመለከተ ወንድ ሥጋ ቸርቻሪ መስለነው ስጋችንን እንድንሸጥለት ጠይቆናል …. የእኛ ማንነት ግን መሸጥ መለወጥ አልነበረም …. ማንነታችን ግን መባከን አልነበረም…. ሱሪውን አውልቀን ቀሚስ ብናጠልቅ ጊዜ ያው የሥጋ ደንበኛ ሥጋ እንድንሸጥለት ብሮችን ዘርዝሯል …. የኛ ዓላማ ግን ሥጋ መሸጥ አልነበረም…. ቀዳዳውን መድፈን  እንጂ …. የሃንድ አውት ስንባል እንዳንሳቀቅ …. ለዝግጅት ስንባል እንዳናፍር ነበር …. እውነቴን ነው የምለው የምንሆነውን ሳይሆን የማንሆነውን ነው የሆነው …. ታዲያ ለአንዳንዶቻችን ተገላቢጦሽ ለሆነብን ሕይወት---- ከጥቁር ወዲያ የሚገልፀው ምን አለ?
የሞዴስ መግዣ  ቸግሮን …. ከዶርም መውጣት አሳፍሮን፣ ተሸሽገን ቀናቶችን አሳልፈናል …. ሃንድ አውት ኮፒ የምናደርግበት ሳንቲም አጥተን ተውሰን አንብበናል …. አሊያም ምንም ሳናነብ ወደ ፈተና ገብተናል …. አዳሜ በምላሱ ተማምኖ  ግሬድ  ሲያስጨምር፣ የእኛ ምላስ ደርቆ ውሃ ሳያነሳ ሲቀር ፅልመት ወርሶናል …. አልጋ ላይ ሲወጡ ኤ፣ ከአልጋ  ላይ ሲወርዱ ኤፍ ከሚሉት መምህራን ጋር አንዳንዶች አንሶላ ሲጋፈፉ …. እኛ ግን ለሚያልፍ ቀን ብለን …. ለክብራችን ብለን …. የአልጋ ላዩን ጨዋታ…. የአልጋ ላዩን  ዕቃቃ …. አንቀበልም ብንል ጊዜ የሚተማመኑበትን በትር ሰንዝረውብናል …. ለዜሮ ነጥብ አምስት A ማግኘት እያለብን ሳናገኝ …. B ማግኘት እያለብን ሳናገኝ፣ ሴሚስተሩን በሙሉ ጨጓራችን እየበገነም ቢሆን ሁሉን አልፈነዋል …. ማለፊያ ነጥብ ሞላልኝ አልሞላልኝ እያልን ለተሳቀቅንባቸው …. ለእነዛ ሴሚስተሮች መልበስ  የሚገባን ጥቁር ልብስ ነው …. አንድ ከአርባ (1/40) …. ሁለት ከአርባ (2/40) ….ሦስት ከአርባ (3/40)  ለሰጡን መምሕራን …. በቦክስ ለመቱን መምህራን …. ዓለም ያልደረሰበት ሚስጢር በእጃቸው ያለ ይመስል ከመጠን በላይ ለተኮፈሱብን ለእነዛ መምህራን --- መልበስ ያለብን ልብስ ቢኖር ጥቁር ነው….
የተናገርነውን ንግግር ትርጉሙን ለጠመዘዙብን ኃላፊዎች…. ለማየት ከምንጓጓለት ቦታ ላስቀሩን …. የአስተዳደር አካላት….የተሻለ አስተሳሰብ ሲቀርብ ለሚደነግጡት…. ቆይ እንወያይ…..ወዘተ እያሉ ጊዜ ለገደሉብን ለእነርሱ መልበስ የሚገባን ጥቁር ልብስ ነው …. አዎን ጥቁር የምንለብስባት ያቺ የምርቃት ቀናችን በሕይወታችን ብዙ ነገር መከናወኑን የምትነግረን ነች ….. ነጭ የለበስንበት የቀለም ቀናችንን (colour day) የምትቀማን ናት…..
አዎን በቀለም ቀናችን …. ነጭ ለብሰን በደመቅንበት ቀን …. ፊታችን በሕብረ ቀለም አሸብርቋል …. ቲ-ሸርታችን በአባባል ደምቆ …. ወንድምነታችን እህትነታችን አይሎ የወጣንበትን የቀለም ቀን የምትቀማን ቀን ነች…. አዎን በዛች ቀን ያሻነውን ፅፈናል፤በፈለግነው ሙዚቃ ዘፍነናል …. ይሄ አንገት ነው …. ምን ታፈጣለህ…. ምን ታፈጫለሽ ….ታስጨርሰኛለህ…. እንወድሀለን …. እንወድሻለን…. ሴት ልጅ ደሀ የምትወደው ፊልም ላይ ብቻ ነው …. ብልጭ እና ቁልጭ…. U R Z Best …. እንዳትረሱኝ …. ሲጋራውን አፕላይ…. የተባባልንበት የቀለም ቀናችንን የምትቀማን ቀን ነችና እባካችሁ በምርቃት ቀናችን ጥቁር እንልበስ …. ነጭ  እንደሆነ ብርሀን ነው፡፡ ነጭማ ከዋሻው ጫፍ ለመድረሳችን ምልክት ይሆነን ዘንድ የተሰጠንን ማህተም ነው፡፡ ነጭማ ትንሣኤ ነው፤ የትዝታ ድንጋዮችን የሚፈነቅል የትዝታ መቃብሮችን በደስታ የሚያሸንፍ፤ ወንድምነታችንን የሚያድስ፣ እህትነትን የሚዘክር፤ መዋደዳችንን የሚሰብክ ነው፡፡ ነጭማ ንፁህ ባህሪ ነው፡፡ ነጭማ እንበለ ሙስና ነው። እንበለ ድካም ነው፡፡ እንበለ ህማም ነው፡፡ እንበለ ፃማ  ነጭማ  አሐዱ ውእቱ ነው፤ በቃ ማፍቀር ብቻ፤ መደሰት ብቻ፤ ተዋዶ ተሳስቦ መኖር ብቻ ነው። አሸብሽቦ መዝሙር  ነው፡፡ ለነገ ትውስታ እጅ ለእጅ ተያይዞ፣ አንገት ለአንገት ተቃቅፎ  ፎቶ  መነሳት ነው፡፡ ቲ-ሸርት በዲፓርትመንት ማሰፋት ነው፡፡
ነጭማ ሕመም የለውም፤ አይጎረብጥም አይሻክርም፤ እንቅፋት የሌለበት የሜዳ ላይ ጉዞ ነው። ጥቁር  ግን ብዙሃን ባህሪ  ነው፡፡ ጥቁር መለየት ነው፤ ጥቁር መሰደድ ነው፤ ጥቁር እንደ ቀራንዮ ጉዞ በመውደቅና በመነሳት የታጀበ ነው፤ ህመማችን የተፃፈበት የደም ልብሳችን  ቢኖር ጥቁር ልብስ ነውና እባካችሁን ጥቁር እንልበስ፡፡
አፍሮ  ጸጉር ሆነን ገብተን ራስ በራ ሆነን የምንመረቀው እኛ ጥቁር እንልበስ፡፡ ሃይማኖተኛ ሆነን ገብተን ጀነግ /ጀዝብ ነፃነት ግንባር/ ሆነን ለወጣን እኛ መልበስ የሚገባን ልብስ ጥቁር ነው። ቁጭት ሆድ አስብሶን እግራችን ፈርከክ አድርገን የአረቄ ብትሌ እያነሳን ለለጋንባቸው ቀናቶች፣ ጠጅ ለጠጣንበቸው ለእነዛ ቀናቶች መልበስ ያለብን ጥቁር ልብስ ነው፡፡
በምርቃት ቀን የምንለብስው ልብስ የሚናገርልን ነገር ቢኖር ያለፈ ታሪካችንን ነው፡፡
አንድ ዓመት ወደ ኋላ ተመልሰን /Readmission student/  የተማርንበትን የጊዜ ወሰን የሚገልፅ ነው፡፡ ያ ልብስ የሚነግረን በተጫርን ጊዜ፤ አንድ ሴሚስተር ወደ ኋላ በተባረርን ጊዜ ፤ወደ ቤት መሄድ አፍረን ጎንበስ ቀና እያልን ያስተናገድንባቸው ካፌዎችን ነው። ወደ ቤት ላለመመለስ ስንል ብቻ አስተናጋጅ ሆነን የተሸሸግንባቸውን  ሆቴሎች የሚዘክር ነው፡፡ ጥቁርማ ከእኝ እኩል በምርቃት ቀን በሱፍ፣ በከረባት፣ በፎቶ ሊደምቁ ያልችሉትን፣ ሞት የቀደማቸውን ተፈጥሮ ክንዷን ያበረታችባቸውን፣ አፈር ያንተረሰችባቸውን፣ በሞት የተለዩን ወንድሞቻችን እህቶቻችን የሚዘክርልን ልብስ ነው። በዩኒቨርስቲ ቆይታችን አብረን ታድመን፤ ክላስ ላይ ተምረን፣ ካፌ ተመግበን፣ አብረን አጥንተን፣ ያንን ሁሉ  ዓመት የማዕበሉ ጊዜ አሳልፈን፤ ነገር ግን ዛሬ ላይ ጥቁሩን ልብስ ለመልበስ ላልታደሉት ወንድሞቻችን  እኛ መልበስ የሚገባን የእነርሱን ጥቁር ልብስ ነው፡፡ በጥቁር የሚጻፍ እውነታ ምንግዜም ቢሆን አይሻርም፤ እኛም  እነሱም ጥቁር እንልበስ እስኪ፤ ማን ነው በየዓመቱ  የሞትን መርዶ ሳይሰማ እዚህ የደረሰ? እስኪ የቱ ነው በቆየንባቸው አምስት ዓመታት ለሞቱት ወገኖቻችን አንፊ ላይ ቁጭ ብሎ በሕሊና ጸሎት ያልተከዘ፣ ሻማ ያላበራ፣ ጧፍ ያለኮስ፣ እስኪ ማን ነው?
ያቺ የምርቃት ቀን እጅግ አብዝተን የምወዳቸውን ፍቅረኞቻችን የምትነጥቀን ቀን ነች። ስትስቅ  የምወደውን እርጋታዋን፣  አስተሳሰቧ የሚማርኩኝ ያቺን የከንፈር ወዳጄን የምትቀማኝ ቀን ነች፡፡ ጥቁር ከምለብስበት የምርቃት ቀን በኋላ የከንፈር ወዳጄ ምክር የለም፤ እሷ ከአድማሳት ወዲያ እኔ ከአድማሳት ወዲህ መለያየት  ዕጣ ፈንታ ውስጥ እንወድቃለን፤ ከዛች ቀን በኋላ ትዝታን ብቻ  በጥቁር ልብስ ውስጥ እየወዘወዙ እንደ ክራር እየጠዘጠዙ፤ እንደ በገና እየደረደሩ፤ በምልክት ጥይት ውስጥ ትዝታን ከተው በሰመመን ሩጫ መጋለብ ብቻ። ሌላ  አንዳች የሚፈጥሩት ነገር ላይኖር ብቻ ዝም ብለው ሊሸረክቱ  ብቻ፣ ዝም ብለው ሊያለቅሱ ፣ ብቻ  ዝም  ብለው ዝም ለሚሉባት  ለዛች መናጢ ቀን መልበስ ያለብን ልብስ ቢኖር  ጥቁር ነው፡፡ እናም  ጥቁር እንልበስ፡፡
አንተስ ብትሆን፤ አንቺስ ብትሆኚ ሰላሳለፍከው፣ ስላሳለፍሽው  የፍቅር ዘመናት መልበስ የሚገባሕ/ሽ ጥቁር ልብስ ነው፡፡ እሷን ለመናገር  ላፈርክባቸው ቀናት፣ እሷን ስታስባት ደረት ለደለቀው ልብህ ለመታው ለዛች ቀን ምን ይሆን የምትለብሰው? ፍቅረኛህን እንደምትለያት የተማርክበት ጊቢ ሲነግርህ  የሕይወት  ዑደት መለያያት መሆኑን ስታውቅ ምን ትለብስ? መለያየት በአንተ ዘንድ ዋጋ ከሌለው ነጭ ልበስ፣ መለያየት ለአንተ ለአንቺ ዋጋው ብላሽ ከሆነ፣ ትርጉም ከሌለው፣ ውሃ የሚያነሳ  ከሆነ ነጭ ልበስ፡፡  መለያየት ግን ትርጉም ካለው፣ መነፋፈቅ ተገናኝቶ መበታተን፣ ባህሪን ተላምዶ ማን ምን እንደሚያስደስተው፣ ምንስ  እንደሚያስቀይመው አውቆ፣ ዳግም ላይገናኙ መበታተንን ከተረዱ፣ አንተም አንቺም፣ እኛ ሁላችን የመለየትን መጥፎነት ከተረዳን እባካችሁ ጥቁር እንልበስ፡፡ የፍቅረኛሞችን መንገድ ልንረሳው ነው…. ቁጭ ብለን እያወጋንባቸው በዛፍ የተከበቡ ጨለማ የዋጣቸው እነዛ  የፍቅረኛሞች መቀመጫን ልንረሳቸው ነው፡፡ እስኪ እና ሁላችን በምርቃት ቀናችን ጥቁር አንልበስ፡፡
ያቺ ቀን የማትቀማን ሁልጊዜ ዕሮብ ዕሮብ እየተሰባሰብን የስነጽሁፍ አምሮታችንን የምናስታግስባትን ምሽትን ነው፡፡ በተለይ ለእኔ የምታስቀርብኝ ነገር  ቢኖር ብዙ ነው፡፡  ፍቅር ባጣ ዪኒቨርስቲ ውስጥ ስነጽሑፍ በፍቅር አንድ ያደረገችን፣ በግጥም በወግ በድራማ  የተሳሰርን አንድ የሆነ እኛ ---- ፍቅር እርሷ ፈትላ እርሷ ባዝታ፣ የደደረውን ማንነታችን  ነቅሳ፣  ጥፍጥሬውን ጥላ የገመደችን የሻሸመኔ መደወሪያ በሚመስለው የፍቅር መርከቧ ከአንዱ ጥግ ወደ አንዱ በሃሳቦች፣ በጽሑፎቻችን አስጉዛ ለብርድ ብላ ያዘጋጀችን ኩታ ነን፡፡ እናም ከዚህ ውህደት ውስጥ ተለይቶ መኖር ይከብዳል፡፡ እናም እናንተን የስነጽሑፍ ወዳጆቼን ሳስብ ውስጤ ጥቁር ልበስ ልበስ ይለኛል፡፡ በጥቁር ተሞሸር ይለኛል፡፡ ቢጫ አለብስ ነገር ጨነቀኝ፤ ቢጫ ፍካት ነው፤ እንደፈካን  ደግሞ መች እንኖርና! አረንጓዴ አለብስ  ነገር  ልምላሜ ነው፡፡ ጓደኝነታችን መለያየት ሲገባን፣ ልምላሜው ይከስማል፡፡ ነጭ እንዳልለብስ ነጭ ደስታ ነው፡፡ ያለኝ ብቸኛ አማራጭ ጥቁር መልበስ ነው፡፡ እናም በዛች የምርቃት ቀን ጥቁር እለብሳለሁ፤ እናንተስ ምን ትለብሱ ይሆን? እባካችሁ ጥቁር እንልበስ፡፡
ከዓመታት በኋላ ስንገናኝ በተስፋ እንታደሳለን፤ ብርሃን የሆነውን ነጭ ልብስ እንለብሳለን፡፡ ያኔ ተገናኝተን “አንተ አለህ  አንቺ አለሽ ወይጉድ” አስክንባባል ድረስ ጥቁር እንልበስ፡፡ አዎን እስከዛ ድረስ  በጠቆረ  ልብስ፣  የጠቆረ ማንነታችንን እንግለፀው። ጊዜ አገናኝቶን ለሚለየን፣ ለለያየንም ለእኛ ለዚህ ዓመት ተመራቂ ተማሪዎች ጥቁር እንልበስ፡፡ ጥቁር ይሁን ቃልኪዳናችን፤ ጥቁር ይሁን ውላችን፡፡ ጥቁር ለመገናኘታችን ዋስትና ይሁን፡፡ ጥቁር፤ ስንገናኝ ነጭ ለመልበሳችን ዋስትና ይሁነን፡፡
እውነት ነው፤ ጊዜ እየተፍገመገመ ወደ እኛ እየቀረበ ነው፤ ሰቀቀን ሊገለን ነው፡፡  ሙሾ  ሊከበን  ነው፤ አበባ  ታቅፈን ልናነባ ነው፤ በጥቁር ልብስ  ልንሞሸር ነው፤ መመረቃችን ለእኛ ሞት ነው፡፡ ለዛም ነው የምናለቅሰው፤ ለዛም ነው ሆዳችንን ባር ባር የሚለው፤ ለዛም ነው ጥቁር የምንለብሰው። ለሁሉም የቸርነት አምላክ እርሱ አይለያየን፤ የአንድነት አምላክ ፍቅርን ይስጠን፡፡ ኪሎ ሜትሮችን ሳይገድቡን፣ አድማሳት ጋራዎች ሳይከልሉን እንደንጠያየቅ ያድርገን፡፡ መለያየት  ያለበሰንን ጥቁር ልብስ፤ ትዝታውን የምንችልበት ትከሻ ይስጠን፡፡
የፍቅር አምላክ የጨከኑባችሁን  የፍቅረኞቻችሁን ልብ አራርቶ፣ በአንድነት ጥላ ውስጥ ያስጠልላችሁ። አንድ ሆናችሁ መለያየት ላይ ፎክሩበት፤ አቦ ይመቻችሁ፡፡ የእናታችሁ ምርቃት አይለያችሁ፡፡  ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!
እኛም ለዘላለም እንኑር!!                               

  የቤተሰብ ምጣኔ ወይንም እቅድ ማለት ትርጉሙ አንድ ቤተሰብ የሚፈልጉትን ያህል ልጅ በሚፈልጉበት ጊዜ መውለድ እንዲችል የሚያግዝ የህክምና አገልግሎት ማለት ነው። ይህን የተናገሩት ዶ/ር ደመቀ ደሰታ በአይፓስ ኢትዮጵያ የፕሮግራም ማናጀር ናቸው።
ባልና ሚስት የተለያዩ እቅዳቸውን እስኪያከናውኑ ድረስ መውለድ ካልፈለጉ የሚቆዩበት ወይንም የተወሰኑ ልጆችን ከወለዱ በሁዋላ በቃን ከዚህ በሁዋላ ልጅ መውለድ አንፈልግም ሲሉ እንዳይወልዱ ማገዝ ማለት ነው። ይህ እንግዲህ በቤተሰብ ደረጃ ከተጣመሩ ወይንም ከተጋቡ በሁዋላ ያለው ሲሆን ሌላው ደግሞ ሰዎች በግላቸውም የሚኖሩበት ሁኔታ ስላለ ያልተፈለገ እርግዝናን መከላከያ መጠቀም እንዲችሉ ይደረጋል። ለብቻ የሚኖሩ ሰዎች የሚጠቀሙበት መንገድ መጸነስ እንዳይችሉ ወደሚለው ትርጉዋሜም ይሄዳል። ይህንን መወሰን የሚጠቅመው ለምንድነው ወደሚለው ጥያቄ ስንሄድ አንድ ቤተሰብ መውለድ ያለበት ማብላት ማጠጣት ማልበስ ማስተማር የሚችለውን ልጅ ያህል መጥኖ እንዲወልድ ለማድረግ እና ሙሉ ዜጋ አድርጎ ማሳደግ እንዲችል ነው። ቤተሰቡ አቅሙ ትንሽ ሆኖ ሊያሳድገው ከሚችለው በላይ ልጅ ከወለደ በበቂ ሁኔታ መግቦ እና አልብሶ አስተምሮ ማሳደግ ስለሚሳነው የተወለደው ልጅ በትምህርቱ ውጤታማ እንዳይሆንና ወደተሸለ ሕይወት እንዳያመራ እንቅፋት ይሆንበታል። ያ ቤተሰብም ወደባሰ ድህነት ይወርዳል። ይህ በሀገር ደረጃም ሲታይ መንግስት ማሟላት የሚባቸው እንደትህርትቤት የጤና አገልግሎት መንገድ የመሳሰሉት ሁሉ የሚጠበቅበት ከሆነ መጠነኛ ገቢ ያለው እና ብዙ ሰው የሚያስተናግድ መንግስት ከሆነ አገልግሎቱንም ማዳረስ ስለሚሳነው እራሱ መንግስትም የድህነቱ ተቋዳሽ ይሆናል።
በፈረንጆቹ አቆጣጠር July 2012 ነበር በለንደን ስለቤተሰብ እቅድ ሀገራት በአዲስ መልክ የሚያስፈጽሙትን በተመለከተ ቃል የሚገቡበት አለም አቀፍ እቅድ የተነደፈው:: በዚህ ረገድም ሀገራት ውጤታማ በሆነ መንገድ ብዙም አቅምን በማይፈታተን መንገድ እርምጃ ለመውሰድ የየራሳቸውን ትልም ተልመዋል። ኢትዮጵያም በ2014 አጋማሽ በኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ስር በሚገኘው የእናቶችና የሕጻናት ጤና ዳይሬክቶሬት አማካኝነት ከ2015-2020 ድረስ የሚፈለገውን ስኬት ለማስመዝገብ እየሰራች ትገኛለች። በፈረንጆቹ አቆጣጠር May 2015 የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የቴክኒክ ድጋፍ ከሚያደርገው ቡድን ጋር በመሆን በተቀናጀ መልክ ሁኔታው እንዲታይ አድርጎአል።
ስለዚህ የጤናና የልማት ተሳታፊዎች ተባባሪዎች እና የቤተሰብ እቅድ ዘዴ ባለሙያዎች እንዲሁም አማካሪዎች ጁን 2016 ከብሔራዊው የስነተዋልዶ ጤና እቅድ ጋር በሚጣጣም መልኩ ስራው እንዲሰራ አስፈላጊውን ድጋፍ አድርገዋል። የቴክኒክ ድጋፍ የሚያደርገው አካል ከ30 በላይ የሚሆኑ በስራው የሚሳተፉ አካላትን በማጋገርና ከ20 በላይ የሚሆኑ አማካሪዎችን ከሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ኃላፊዎች እና አብረዋቸው ከሚሰሩ በ9 የክልል መስተዳድሮች እና ከአዲስአበባና ድሬደዋ ጋር እንዲገናኙ በማድረግ በአንዳንድ አስፈላጊ ነጥቦች ላይ አትኩረዋል።
የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት በግል ደረጃ ምን ያህል አስፈላጊ ነው ስንል ላነሳነው ጥያቄ ዶ/ር ደመቀ የሚከተለውን መልስ ሰጥተዋል። “…በግል ደረጃ ድሮ እንደሚታወቀው በሀይማኖትም ይሁን በባህል ወንዶችም ሆኑ ሴቶች ከጋብቻ በፊት ወሲብ እንዲፈጽሙ አይደገፍም ነበር። አሁን ግን በፈቀዱ ጊዜ ወሲብ መፈጸም እንደነውር ከማይቆጠርበት ዘመን ላይ ደርሰናል።ነገር ግን ማንኛውም ሰው እራሱን ለመቻል እንደድሮው ከቤተሰብ የሚወረስ ወይንም የሚገኝ ሀብት ብዙም ባለመኖሩ ሁሉም ሰርቶ ጥሮ ግሮ እንዲያገኝ ከሚገደድበት ደረጃ ላይ የሚገኝ ነው። ለዚህም አስቀድሞ መማር አንድ መመዘኛ ሲሆን ነገር ግን አንዲት ሴት ልጅ ለምሳሌ ወደሁለተኛ ደረጃ ስትደርስ ወይንም ዩኒቨርሲቲ ስትደርስ እርግዝና ቢከሰትባት ትምህርቱዋንም ታቋርጣለች…ስራ ሰሰርቶ ለማደርም የተሸለ እውቀት ሰለሌላት ከዝቅተኛ ደረጃ ላይ እንድትሆን ትገደዳለች።በዚህም ምክንያት የወደፊት ሕይወትዋ ይጨናገፋል። ይህች ልጅ በቤተሰብ ተቀባይነትን ማጣት ልጅዋን ለማሳደግ አቅም ማጥት የፍቅር ጉዋደኛዋ የነበረ ሰው ትኩረትን ማጣት በመሳሰሉት ምክንያቶች ሕይወትዋን እንድትጠላ ትገደዳለች። አንዳንዶች ይህንን በመፍራት አስቀድሞውኑ ጽንሱን ደህንነቱ ባልተጠበቀ መንገድ ወደማቋረጥ ስለሚሄዱ ሕይወትን እስከማጣት የሚደርሱበት ሁኔታ ይከሰታል። ወንዶቹ ግን ምንም እንኩዋን የጉዳዩ ባለቤቶች ቢሆኑም አርግዘው አይታዩም ትምህርታቸውንም አያቋርጡም በቤተሰብ ዘንድ ውግዘት አይደርስባቸውም ። ነገር ግን ድርጊቱን የፈጸሙ በመሆናቸው ኃላፊነት ሊወስዱ ይገባቸዋል። ስለዚህ እንደዚህ ካለው ችግር ከመውደቅ በፊት ፍቅረኛሞች ተመካክረው ወሲብ ከመፈጸማቸው በፊት ያልተፈለገ እርግዝናን ለመከላከል የሚያስችል አገልግሎት ማግኘት ይገባቸዋል። ” ብለዋል።
የኢትዮጵያ መንግስት 2015-2020 የአምስት አመት እቅድ የህብረተሰቡን ጤናና ደህንነት ለማሻሻል ራእይ አለው። የዚህም እቅድ አንዱ ማስፈጸሚያ ተደርጎ የተወሰደው የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት በተገቢው ለህብረተሰቡ መስጠት ነው። በዚህም የተነሳ ኢትጵያ በውጭው አቆጣጠር እስከ 2020 ዘመናዊ የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎቱን መጠን ወደ 55% ማሳደግ ትሻለች። ይህንንም ተግባራዊ ለማድረግ ያልተፈለገ እርግዝና መከላከያ በትክክል መገኘት መቻልø ወደትግበራው ሲገባ አስፈላጊው የሰው ኃይል እንዲኖር፣ የጤና አጠባበቅ መመሪያ መኖር፣ ፖሊሲ፣ ምጣኔ ኃብት እና ምቹ ሁኔታን ስለመፍጠር አስፈላጊውን መመሪያ ማግኘት በህብረተሰቡ ዘንድ ማህበራዊና ባህሪያዊ ለውጥን ለማምጣት የሚያስችል ግንኙነት መፍጠር፣ ለወጣቶች ግልጽ እና ቅርብ የሆነ ቀለል ባለ መንገድ የስነተዋልዶ ጤናቸውን እንዲጠብቁ ድጋፍ ማድረግ …ወዘተ የመሳሰሉትን በሚመለከት ቅድመ ዝግጅት ተደርጎአል።
ፍላጎትን መፍጠር፡-
ሰዎች የቤተሰብ እቅድ ዘዴን በተለይም ለረጅም ጊዜ ዪያገለግለውን ፈልገው እንዲጠቀሙ በማድረግ አገልግሎቱንም በቀላሉ ሊደረስበት በሚችል መልኩ ማመቻቸት እንዲሁም ትክክለኛውን መረጃ እንዲያገኙ ማድረግ ነው።
አቅርቦትና አገልግሎት፡-
በሙያው የተሰማሩ ጥራት ያለው ያልተፈለገ እርግዝናን መከላከያ ማቅረብ እንዲችሉ፣ እንዲሁም ሁሉም ተጠቃሚዎች መድሀኒቶቹን የማግኘት እድል እንዲኖራቸው በተለይም ወጣቱ እና አርብቶአደሮች ተገቢውን ደረጃ በጠበቀ መንገድ እንዲሁም በሪፈራል እና ተንቀሳቃሽ ክሊኒኮች አማካኝነት እንዲሁም ለአዋቂዎችም ሆነ ለወጣቶች ተስማሚ የሆነ የስነተዋልዶ ጤና አገልግሎትን እውን ማድረግ ነው።
የኢትዮጵያ ሕዝብ ቁጥር በ1960 ዓ/ም 22.2 ሚሊዮን የነበረ ሲሆን ይህ ቁጥር በ2015 ወደ 90 ሚሊዮን አድጎአል። የኢትዮጵያ ሕዝብ ቁጥርም በየአመቱ 2.6% ሲሆን በዚህ ከቀጠለ በ2020 የህዝቡ ቁጥር ወደ 112 ሚሊዮን ይደርሳል ተብሎ ይገመታል። የመዋለድ ቁጥር ግን በ200 ዓ/ም 5.9 የነበረ ሲሆን በ2014 ግን 4.1 ተመዝግቦአል። ይህም የመዋለድ ደረጃው ቀስ በቀስ እየቀነሰ መምጣቱን ያሳያል። ምናልባትም በየቤተሰቡ የልጆች ቁጥር መጨመር ከተለመደው የጋብቻ አይነት ማለትም በብዙው ቦታ ሴቶቹ በወጣትነታቸው ስለሚያገቡ ብዙ ልጅ ይወልዳሉ የሚል እምነት አለ። በትዳር ከመጣመር ውጪም በርካታ ልጃገረዶች ትምህርታቸውን እያቋረጡ ልጅ የሚወልዱ ሲሆን ከዚህም በተጨማሪ ብዙዎች ደግሞ ካለው የመከላከያ አቅርቦት ችግር ያልታቀደ እርግዝና እንደሚገጥማቸው መረጃዎች ይጠቁማሉ።
ዶ/ር ደመቀ እንደሚገልጹት የጤና ኤክስቴንሽን ስራ ዋና አላማ ከማከም ይልቅ በመከላከል በሽታዎችን ማስቀረት እንችላለን የሚል ስለሆነ በህብረተሰብ ውስጥ ገብተው ያልተፈለገ እርግዝናን መከላከል ላይ እየሰሩ ይገኛሉ። ያ ፕሮግራም ከተጀመረ ወዲህ ብዙ ለውጥ ወይንም እድገት ታይቶአል። በእርግጥ ይህ ተፈላጊው ደረጃ ላይ ደርሶአል የሚያሰኝ አይደለም። በ2016 ባገቡ ሴቶች ላይ የተጠናው ጥናት እንደሚያሳየው የቤተሰብ እቅድን መጠቀም እንፈልጋለን ብለው አገልግሎቱን ያገኙት 36 ከመቶ ናቸው። ይህ ቀድሞ ከነበረው ጋር ሲነጻጸር ጥሩ ቢሆንም አሁንም ግን ዝቅተኛ ነው። በሌላም በኩል በዚሁ ጥናት የተገኘው የቤተሰብ እቅድ አገልግሎትን መጠቀም ፈልገው ማግኘት ያልቻሉት አሁንም ቁጥራቸው ወደ 23 ከመቶ ስለሆነ ብዙ ነው። ወደ 9 ከመቶ የሚሆኑት ከዚህ በሁዋላ ልጅ ማርገዝ የማይፈልጉ ወይንም ደግሞ ቋሚ የእርግዝና መከላከያ መጠቀም የሚፈልጉ ሲሆኑ አገልግሎቱ ግን አልደረሰላቸ ውም።በህብረተሰቡ ዘንድ ግንዛቤው ግን በጥሩ ደረጃ ነው ማለት ይቻላል።

 (እኻ ቲያፈኳን ኧኳዳር አት ኧደንግር ባነ ባረም) የቤተ ጉራጌ ተረት
ከኤዞፕ ተረቶች አንዱ እንዲህ ይለናል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ሰው ክፉኛ ይታመምና ቤቱ ይተኛል፡፡ የመንደሩ ሰው ሁሉ የሚበላም የሚጠጣም እያመጣ በየተራ ይጠይቀዋል፡፡
“አቶ እገሌ” ይላል ጠያቂ
“አቤት” ይላል ተጠያቂ
“ዛሬስ እንዴት ነህ?”
“ከትላንቱ ይሻለኛል”
“ሐኪም ዘንድ ሄደህ ነበር?”
“አልሄድኩም”
“ታዲያ ከትላንቱ እንደተሻለህ በምን አወቅህ?”
“የታመምኩት እኔ አይደለሁ፤ ሰውነቴ ይነግረኛልኮ”
“ደህና እንኳን ለዚህ አበቃህ!”
ጠያቂዎቹ ተሽሎታል ብለው ሰውየውን ለመጠየቅ መምጣታቸውን ያቆማሉ፡፡ ሰውዬው ግን ካልጋው አልተነሳም፡፡ “እስቲ እንሂድና እንየው፤ ይሄ ሰው ለምን አልተነሳም” ብለው ቤቱ ቢሄዱ እዚያው እንደተኛ አገኙት፡፡
“አያ እገሌ” ይላል ጠያቂ
“አቤት” ይላል ተጠያቂ
“ዛሬስ እንዴት ነህ፤ እኛኮ ተሽሎኛል ስትል ትነሳለህ ብለን ነው የቀረነው፡፡ ዛሬ እንዴት ነህ?”
“ከትላንቱ ይሻለኛል”
“ባለፈውም ዛሬ እንዴት ነህ ስንልህ ከትላንቱ ይሻለኛል ብለኸን ነበር፡፡ እንዴት ነው ነገሩ?”
“እዚህ አገር ከትላንቱ ይሻለኛል የማይል ማን አለ?”
“እንደዚህ ከሆነ ሐኪም ቢያይህ ነው የሚሻለው” ብለው ሐኪም ይጠሩለታል፡፡ መድኃኒት አዞለት ይሄዳል፡፡ መድኃኒቱን ይወስዳል፡፡
በነጋታው ሐኪሙ ይመጣል፡፡
ሐኪሙ - “እንዴት ነህ?” ይለዋል፡፡
በሽተኛው - “ደህና ነኝ ዶክተር፤ ግን በጣም ያልበኛል”
ሐኪሙ - “ይሄ በጣም ጥሩ ምልክት ነው” ይለውና ይሄዳል፡፡
በሚቀጥለው ሐኪሙ ይመጣል፡፡
“እህስ አሁንስ እንዴት ነህ?” ይለዋል፡፡
በሽተኛው - “ተሽሎኛል፤ ግን እዚህ መገጣጠሚያዬ ላይ ይቆረጥመኛል፡፡ ያንቀጠቅጠኛል፡፡ ከዚያ ሰውነቴ በሙሉ በረዶ ይሆናል፡፡”
ሐኪሙ - “ይሄም በጣም ጥሩ ምልክት ነው” ብሎት ይሄዳል፡፡
ሐኪሙ ሌላ ቀን ይመጣል፡፡
“እህ ዛሬስ እንዴት ነህ?” ይለዋል በሽተኛውን
በሽተኛው - “ደህና ነኝ ግን አሁን ደግሞ ኃይለኛ ትኩሳት ለቆብኛል” ብሎ ይመልሳል፡፡
ሐኪሙም - “ኦ ይሄም በጣም ጥሩ ምልክት ነው፡፡ በጣም እየተሻለህ ነው ማለት ነው” ብሎት ይሄዳል፡፡
ከሠፈሩ ሰው አንዱና ወዳጁ የሆነው ሰው ከህክምናው በኋላ ምን ለውጥ እንዳመጣ ሊጠይቀው ይመጣል፡፡
ጠያቂ - “እሺ አያ እገሌ፡፡ ሐኪሙ ካየህ በኋላ እንዴት ሆንክ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
በሽተኛውም - “ወዳጄ አያድርስብህ፡፡ ‹በጣም ጥሩ ምልክት› ሊገለኝ ነው!”
*   *   *
እየተሻለኝ ነው እያለ ከሚሞት፣ “በጣም ጥሩ ምልክት ነው” እያለ ከሚገድል ይሰውረን፡፡ ደግ ደጉን ማውራት የተሻለ ዓለም ለማየት ይጠቅማል የሚለው ብሂል እንደተጠበቀ ሆኖ፤ እየከፋ ያለን ጉዳይ እየተሻሻለ ነው ማለት ግን እያወቁ ማለቅ ዓይነት ነው፡፡ ዕውነቱን ተናግሮ የመሸበት ማደር ለአገርና ህዝብ ይበጃል እንጂ ጐጂ አይደም፡፡ “የማይሰጋ ተስፋ የሌለው ሰው ነው” ይላሉ ፈረንጆች፡፡ “አይመጣምን ትተሽ ይመጣልን ጨምሪበት” የሚሉት ነው አበሾች፡፡ በየኑሮ መስኩ ያለውን ህመም፣ በየሙያ መስኩ ያለውን ተወሳክ፣ በየፖለቲካ መስኩ ያለውን ወረርሽኝ በጊዜ መመርመር ዋና ነገር ነው፡፡ እኛ የወደድነውን እያጐላን በየሚዲያው ብንለፍፍ ለሀገርና ለህዝብ ፋይዳ ያለው ላይሆን ይችላል፡፡
አንድ ፀሐፊ ስለ ጋዜጠኝነት ሲጽፍ “ዋናው የሙያው ቁልፍ - ነገር…
አስፈላጊውን ነገር ተወዳጅ እንዲሆን ማድረግ ነው፡፡ እኛ ግን የወደድነውን፤ አስፈላጊ ፋይዳ ያለው የማድረግ አደገኛ ተግባር ላይ ነን (Make the important interesting but we are in a danger of making the interesting important) ያለውን በፖለቲካም፣ በኢኮኖሚም፣ በማህበራዊ ዘርፍም መንዝረን ብናየው ይጠቅመናል፡፡
ዕውነትን መናገር በሽታን ከመደበቅ ያድናል፡፡ ሳይሻለን ተሻለን፣ ሳንድን ድነናል ከማለት ያድነናል፡፡ ከትላንት የተማርን ከማስመሰል ያወጣናል፡፡ ሰፈር - ሙሉ ሰው ከማሳሳት ያተርፈናል፡፡
በየዘመኑ ነባራዊ ዕውነታን ለራስ በሚያመች መልኩ በመቅረጽ ዕውነቱ ይሄ ነው እያሉ ለማሳመን መጣር የተለመደ ዘዴ ነው፡፡ ላንዳንዶች የአገዛዝ መላ ነው፡፡ ላንዳንዶች ከጣር ማምለጫ ነው፡፡ ኒክ ዴቪስ የተባለው ፀሐፊ ዕውነት እንዳንናገር የሚያደርጉን ሦስቱ ገዳይ ድክመቶች (1) የምንመርጣቸው ርዕሰ ጉዳዮች ዕውነታውን በመሠረታዊ መንገድ የሚያፋልሱት እንዲሆኑ በማድረግ ዋናውን ጭብጥ ማሳት
2) በተደጋጋሚ የምንጠቀምባቸውን ኢ-ተአማኒ፣ አንዳንዴም ፈጽሞ ውሸት፣ የሆኑ ጭብጦች ደጋግመን በመጠቀም ዕውነተኛ ማስረጃዎች እንዲመስሉ ማድረግ፤
3) ከአካባቢው ህብረተሰብ መካከል ኃይለኛ ጉልበት ያላቸውን ወገኖች የሚያደምቁ ዕሴቶችን የማያቋርጥ አሻራ እንዲኖራቸው ፖለቲካዊና ሞራላዊ ውትወታን ማብዛት፤
ናቸው፤ ይለናል፡፡
ስለ ዛሬ ጤንነታችን ስንጠየቅ ስለ ትናንት በሽታ ብናወራ የምናገኘው ጠቀሜታ ራስ - ተኮር እርካታ ካልሆነ በቀር ደርዝ ያለው ነገር አገር አንጀት ላይ ጠብ አያደርግም፡፡
ራሳችንን ከዛሬ ሥራችን፣ ከዛሬ ትልማችን፣ ከዛሬ ዕውቀታችን፣ ከዛሬ ውጤታችን ጋር እናመዛዝን፡፡ ህዝብ እየወደደኝ ነው እየሸሸኝ፣ እየሰለቸኝ ነው እየረካብኝ፣ የተናገርኩት እንደ ቡመራንግ ተመልሶ እኔኑ እየወጋኝ ነውን? ዕውነተኛ ደጋፊ እያፈራሁ ነውን? ዕውነተኛ ተቃዋሚ አለኝ?
ኢንፎርሜሽን የሥልጣኔ መሠረት የሆነበት ዘመን ላይ ነን፡፡ ኢንፎርሜሽን የሚደብቅ በሽታውን ከደበቀው ሰው አይለይም፡፡
ሌላው ዓለም ዛሬ፤ የህዝብ ግንኙነት ሠራተኞች የዜና ምንጭ ሊሆኑ እንደማይችሉ፣ የመረጃ ፍሰትን እንደሚያደናቅፉ እየተሟገተ መሆኑን አንርሳ፡፡
“የህዝብ ግንኙነት ዲሞክራሲ” (ኤሮን ዴቪስ) በተባለው መጽሐፍ ከጥናት የተገኙ ድምዳሜዎችን እንዲህ ያስቀምጣቸዋል:- “ለሚዲያ ከሚሰጡ መረጃዎች ተለይቶ የሚደበቅ አንድ መረጃ ሁሌ ይኖራል፡፡ በብዙ ድርጅቶች ውስጥ ያሉት የህዝብ ግንኙነት ሠራተኞች ግማሹ ወይም አብዛኛው ሥራቸው፤ ጋዜጠኞች መረጃ እንዳያገኙ ማድረግ ነው፡፡ አንዳንዴም ያለውን እንደሌለ ማድረግ፣ ስለ ድርጅቱ ክፉ ክፉ ወሬ ካለ ጨርሶ መደምሰስ (መሸምጠጥ) ነው ሥራቸው፡፡” ቢሮዎች፣ የቢሮ መሪዎችና ሠራተኞች፤ የፖለቲካ ሰዎች፤ ለኢንፎርሜሽን፣ ኢንፎርሜሽን ቢሉም ለዕውነተኛ ኢንፎርሜሽን፤ በራቸው ክፍት ሊሆን ይገባል፡፡ ልባቸውም እንደዚያው፡፡
ቼስተርተን የተባለው ፀሐፊ ያለውን ነገር ከልባችን ባናወጣው መልካም ነው፡-
“እራት ላይ የሚቀርብ ሙዚቃ፤ ምግብ አብሳዩንም፣ ሙዚቀኛውንም እንደ መስደብ ነው፡፡”
ባንድ ጊዜ ሁለት ተበዳይ ከሚኖርበት ሥርዓት ይሰውረን፡፡ ያም ምግቡ ሳይጣጣምለት፣ ያም ሙዚቃው ሳይሰማለት፣ መቅረቱ የሙያ ብክነት ነው፡፡ ከሁሉም በላይ ግን ከምግቡም ከጥበቡም ያልሆነው የግብር ታዳሚ ህዝብ ያሳዝናል፡፡ ይህንን ልብ ያላለ ታዳሚ ሁለተዜ ጥፋት ላይ ወደቀ ማለት ነው፡፡ ሙዚቀኛ ሳይሰማ እየተሰማሁ ነው ካለ፣ ምግብ አብሳዩ ህዝቡ እየበላ ነው ካለ፣ ታዳሚው ሙዚቃ እየሰማሁ፣ ምግብ እየበላሁ ካለ ተያይዘው ጠፍተዋል፡፡ እየታመመ ተሻለኝ፣ እየተቸገረ ኖርኩኝ የሚል “ሸማኔ ውሃ ሙላት ሲወስደው እስካሁን አንድ እወረውር ነበር አለ” እንደተባለው መሆኑ ነው፡፡ ከ20ኛ ፎቅ ላይ እየወደቀ ሳለ 8ኛ ፎቅ ያሉ ሰዎች እንዴት ነህ? ቢሉት፤ “እስካሁን ደህና ነኝ” አለ እንደተባለው ሩሲያዊ ብናስበውም ያስኬደናል፡፡ “እንዳካሄድ” አደል መንገዱ ሁሉ!

“የልዩ ጥቅም አዋጅ በእውነት ጥያቄውን ይመልሳል?”

በአዲስ አበባ ላይ የኦሮሚያ ልዩ ጥቅምን የሚደነግገው ረቂቅ አዋጅ በሚኒስትሮች ም/ቤት ከጸደቀ በኋላ ለህዝብ ተወካዮች ም/ቤት
መቅረቡ ተነግሯል፡፡ በረቂቅ አዋጁ ላይ ዜጎች እንደሚወያዩበትም ተገልጧል፡፡ ለመሆኑ ረቂቅ አዋጁ በአዲስ አበባና በኦሮሚያ ግንኙነት ላይ
ምን አንደምታ አለው? ከህገ መንግስቱ አንጻርስ እንዴት ይታያል? በዚህ ረቂቅ አዋጅ ላይ የወደፊት ስጋቶችና አደጋዎች ይኖሩት ይሆን? ለምንስ
አነጋጋሪ ሊሆን ቻለ? ምሁራንና ፖለቲከኞች ምን ይላሉ? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤የተለያዩ አስተያየቶችን አሰባስቦ እንደሚከተለው አጠናቅሮታል፡፡ (ለፖለቲካዊ ችግሮች ሁሌም መፍትሄው ፖለቲካዊ ውይይት ነው) ከሚተጉ ሹመኞች፤ የግብር ከፋዩን ገንዘብ መታደግ አለበት፡፡ “

አቶ አሊ አብዱ ሂጅራ (የህግ ባለሙያ)

በሽግግሩ መንግስት ጊዜ የተዘጋጀው የክልሎች አወቃቀር አስራ አራት ክልሎች እንዳሉ የሚያሳይ ነው፡፡ አዲስ አበባም አንዱ ክልል ሆኖ ክልል 14 ይባል ነበር፡፡ በመሰረቱ ኋላ ላይ ዛሬ የምናያቸው 9 ክልሎች የተፈጠሩት ከክልል 7 እስከ 11 የነበሩት በአንድ ተጠቃለው “ደቡብ ክልል” በመባላቸው ነው፡፡ ሁሉም ክልላዊ መስተዳድሮች በመልክአ ምድራዊ ክልላቸው ውስጥ ባሉ ጉዳዮች ሁሉ የህግ አውጪነት፤ የህግ አስፈፃሚነትና የዳኝነት ሥልጣን እንዲኖራቸው ተደርጎ፣ ዋና የበላይ የሥልጣን ባለቤት ግን ማዕከላዊ መንግስቱ ሆኖ ተቋቋመ፡፡
በወቅቱ በአዲስ አበባ አስተዳደርና በሀረር ክልል የኦሮሚያ ልዩ ብሄራዊ ጥቅምና የፖለቲካ መብት የተጠበቀ ይሆናል የሚል ህግ ወጣ፡፡ የእነዚህ ክልሎች ተጠሪነት ለማዕከላዊ የሽግግር መንግስት ሆኖ የመስተዳድሮቹ ግንኙነት በዝርዝር በህግ ይወሰናል ተባለ፡፡ እዚህ ላይ ማስተዋል ያለብን የተደነገገው በአዲስ አበባ ላይ ብቻ ሳይሆን ሃረር ላይም ነው፡፡ እዚህ ህግ ላይ በእንግሊዝኛ ቋንቋና በአማርኛ ቋንቋ የቀረበው ላይ የትርጉም ልዩነት አለው፡፡ በአማርኛው ላይ በኦሮሚያ ክልል እና በሁለቱ አስተዳደሮች መካከል ያለው ግንኙነት በሌላ ህግ በዝርዝር ይወሰናል ይላል፡፡ እንግሊዝኛው ደግሞ በማዕከላዊ መንግስት እና በሁለቱ አስተዳደሮች መካከል ነው የሚለው፡፡ በወቅቱ የተነሳው ስለ “ልዩ ጥቅም” ብቻ ሳይሆን ስለ ልዩ ብሄራዊ ጥቅምና የፖለቲካ መብት ነበር፡፡ ይሄ የሆነው በጥር 1984 ዓ.ም በወጣ፣ አዋጅ ቁጥር 7/84 ህግ ነው፡፡
በ1987 ህገ መንግስቱ ሲወጣ ደግሞ በአንቀፅ 49 የተቀመጠው ጉዳይ አለ፡፡ አንቀፁ ላይ የተቀመጠው ጉዳይ ስለ ክልል የሚደነግግ አይደለም፡፡ አዲስ አበባ የፌደራል መንግስቱ ርዕሰ ከተማ መሆኑ፣ የአዲስ አበባ አስተዳደር ራሱን በራሱ የማስተዳደር ስልጣን እንዳለው፣ አዲስ አበባ ተጠሪነቱ ለፌደራል መንግስቱ መሆኑን፣ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ራሳቸውን ችለው በፓርላማው እንደሚወከሉ ይገልጽና በመጨረሻ ላይ የኦሮሚያ ክልል የአገልግሎት አቅርቦት ወይም የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀምና የመሳሰሉትን ጉዳዮች በተመለከተ፤ እንዲሁም አዲስ አበባ በኦሮሚያ ክልል መሃል የሚገኝ እንደመሆኑ ሁለቱን የሚያስተሳስሩ አስተዳደራዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ያለው ጥቅም ይጠበቅለታል፤ዝርዝሩ በህግ ይወሰናል ነው የሚለው፡፡
እንግዲህ ከአዋጅ 7/84 በኋላ እስከ 1987 ዓ.ም ልክ እንደ ሌላው ራሱን ችሎ ክልል የነበረው አዲስ አበባ፤ ህገ መንግስቱ ሲወጣ፣ ክልል አይደለም የፌደራል መንግስቱ መቀመጫ ግዛት ነው፤ ተጠሪነቱም ለፌደራል መንግስት ነው፤ አዲስ አበባ ራሱን የቻለ የፌደራል መንግስቱ መቀመጫ ነው የሚል ነው፡፡ ይህ ማለት አዲስ አበባ የማንም ክልል መሬት ሳይሆን የፌደራል መንግስቱ ግዛት ነው፡፡ እንደ ናይጄሪያዋ ዋና ከተማ አቡጃ፣ እንደ ዋሽንግተን ዲሲ ማለት ነው፡፡ ማንም የኔ ነው ሊል አይችልም፡፡
ወደ ልዩ ጥቅም ጉዳይ ስንመጣ፤ ቀደም ሲል በሽግግሩ ጊዜ “ልዩ ብሔራዊ ጥቅም” ነበር የሚለው፤ እዚህኛው ላይ ደግሞ “ልዩ ጥቅም” በሚል ነው የተገለፀው፡፡ ሀረር ላይ በሽግግሩ ጊዜ የነበረው አዋጅ ያስቀመጠው በህገ መንግስቱ አልተካተተም፡፡
በህገ መንግስቱ “አዲስ አበባ በኦሮሚያ መሃል የምትገኝ” በሚል ነው የተቀመጠው፡፡ ይሄ ማለት አዲስ አበባ የኦሮሚያ ነች ማለት ነው? በህገ መንግስቱ በግልፅ የተቀመጠውን ጥሠን አንድ ክልል በሌላው ክልል ውስጥ ስልጣን እንዲኖረው ማድረግ እንችላለን? በኔ ትሁት አረዳድ ትግራይ በኦሮሚያ፣ ኦሮሚያ በትግራይ ወይም አንድ ክልል በሌላው ክልል ላይ ስልጣን እንዲኖረው ህገ መንግስቱ አይፈቅድም፡፡ ወንጀለኛ እንኳ ጠፍቶ ሲሄድ የዚያን ክልል ፍቃድ መጠየቅ ወይም ጉዳዩ የፌደራል ስልጣን ነው የሚሆነው፡፡ ግን ይህ ተጥሶ የተደረገበት አጋጣሚ በምሳሌ መጥቀስ ይቻላል፡፡ የጎንደር ፖሊስ ጋዜጠኛ አማረ አረጋዊን አዲስ አበባ መጥቶ ነው የወሠደው፣ በፍቃዱ ሞረዳን አዲስ አበባ ላይ ተሠራ በተባለ ወንጀል የአሶሳ ፖሊስ ነው አዲስ አበባ መጥቶ የወሰደው፡፡ ግን የአሶሳም ሆነ የጎንደር ፖሊስ አዲስ አበባ ላይ ስልጣን አልነበረውም፡፡ ስልጣን ያለው የፌደራል ፖሊስ ነው፡፡
በ1989 የወጣው የአዲስ አበባ አዋጅ ማለትም አዋጅ ቁጥር 87 የሚባለው ምን ይላል? የአዲስ አበባ ህዝብ ራሱን በራሱ ለማስተዳደር ሙሉ ስልጣን እንዲኖረውና ዝርዝሩ በህግ እንደሚወሰን፣ አስተዳደሩ በፌደራል መንግስት የሚወከልበትን የሚገልፅ ህግ ወጣ። ይሄው ህግ አዲስ አበባ ከኦሮሚያ ጋር ስለሚኖራት ግንኙነት ድንጋጌ አውጥቷል፡፡ በዚህ ቻርተር አንቀፅ 2(1) መሠረት፤ የሚከለለው የአዲስ አበባ ወሠን በከተማው መስተዳደርና በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት በጋራ ተለይቶ ምልክት ይደረግበታል፤ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት መቀመጫውን በአዲስ አበባ የማድረግ መብት ይኖረዋል፤ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር ለአዲስ አበባ ህዝብ የሚያቀርባቸው አገልግሎቶች በመስተዳድሩ አዋሣኝ ለሚኖረው የኦሮሚያ ክልል ህዝብ ሊዳረሱ የሚችሉ ሲሆን ነዋሪዎቹ በተመሣሣይ ሁኔታ የአገልግሎቶቹ ተጠቃሚ እንደሆኑ ይደረጋል የሚሉ ድንጋጌዎችን በማስቀመጥ የህገ መንግስቱን ነገር የበለጠ አብራርቶታል፡፡
በዚህ ቻርተር ላይ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር ለአዲስ አበባ ህዝብ ከሚያቀርባቸው አገልግሎች ጋር የተያያዙ የልማት ስራዎችን በኦሮሚያ ክልል መስራት የሚችለው በቅድሚያ ከኦሮሚያ ክልል መንግስት ጋር በመመካከርና በመስማማት ይሆናል ይላል፡፡ ይሄ የጉርብትና ግንኙነቱን ይመለከታል ማለት ነው። በዚህ ሁኔታ ቀጥሎ እያለ በድጋሚ የአዲስ አበባ ከተማ ህግ በጥር 1995 ዓ.ም ተሻሻለ፡፡ በዚህ የተሻሻለ ቻርተር ላይ የከተማዋ አስተዳደር ከኦሮሚያ ክልል ጋር ፍሬያማ ትብብርን መሠረት ያደረገ ግንኙነት ይኖረዋል፤ በህገ መንግስቱ አንቀፅ 49(5) መሰረት፤ የኦሮሚያ ጥቅም የተጠበቀ ነው ብሎ አሁንም ዝርዝሩ በከተማዋ አስተዳደር እና በክልሉ መካከል በሚደረግ ስምምነት ወይም በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት በሚወጣ ህግ ይወሰናል አለ፡፡ በዚያው ዓመት ሐምሌ ወር ላይ ደግሞ በድጋሚ ሌላ አዋጅ ቁጥር 362/95 የሚባል ቻርተር ወጣ፡፡ 6 ወር ሳይሞላ ቻርተር ተቀየረ ማለት ነው፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የይዘት ችግር አለበት የሚል ነበር። በዚህ ቻርተር ላይም የሁለቱን አካላት ግንኙነት በተመለከተ የተቀመጠው ተመሳሳይ ነበር፡፡ እንግዲህ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በአንቀፁ እንደተቀመጠው ነው ያለው፡፡ እዚህ ላይ መነሳት ያለበት በ1984 በወጣው አዋጅ፤ ኦሮሚያ ዋና ከተማው “ፊኒፊኔ” ይሆናል የሚል ተቀመጠ፣ እንደገና በ1987 የወጣው አዋጅ፣ ርዕሰ ከተማውን “ፊኒፊኔ” አደረገ፡፡ ከዚያ በ1994 በወጣ አዋጅ አዋጅ ርዕሰ ከተማው “አዳማ” መሆኗን ገለፀ፡፡ በኋላ አዲስ አበባ ሆነ፡፡  
በአዲስ አበባ ውስጥ ስልጣን የሌለው ክልል ለምንድን ነው አዲስ አበባ ውስጥ ርዕሰ ከተማውን የሚያደርገው? የሚያዝበት ነገር‘ኮ የለውም። የፌደራል መንግስት መቀመጫ የማንም ክልል አይደለችም። አዲስ አበባ የፌደራል መንግስቱ መቀመጫ ከሆነች በኋላ የኦሮሚያ ክልል መቀመጫ መሆኗ ለምን አስፈለገ? የፌደራል መንግስት መቀመጫ የሁሉም ነው መሆን ያለባት፡፡ በኦሮሚያ መሀል መሆኗ ብቻ የኦሮሚያ ነች አያስብላትም። ሌላው ችግር የሁለቱ ክልል ድንበር እስከ ዛሬ በግልፅ አለመካለሉ ነው፡፡
ወደ ልዩ ጥቅም ጉዳይ ስንመጣ የነባር እና የመጤ ህዝብ ጥያቄ የሚነሳ ከሆነ፣ የዚህ ሀገር ባለቤት የአገው ህዝብ መሆን ነበረበት፡፡ እቺ ሀገር የሁሉም ናት፤ የችግራችን መንስኤ ህብረ ብሄራዊነትን መዘንጋትና በብሔረሰባዊ ግቢ ውስጥ የታሰረ “የኔ ብቻ ነው” ባይነት ነው፡፡ ይሄ የልዩ ጥቅም አዋጅ በእውነት ጥያቄውን ይመልሳል? ህዝቡ፣ የፌደራሊዝም ባለሙያዎች በዚህ ጉዳይ ላይ መነጋገር አለባቸው፡፡
ሌሎች ነባር ህጎች የማይፈቱት የአካባቢ አየር ብክለት ጉዳይ፣ የስራ አጥነት፣ የካሣ ጥያቄ ችግር አለብን ወይ? ይሄ የውሸት ቁስል ማከሚያ ነው፡፡ ይልቅ ቁስሉ ምንድን ነው የሚለውን እንመርምረው። የቋንቋ ጉዳይ ከተነሳ ኦሮሚኛ የአዲስ አበባ ብቻ ሳይሆን ለምን በመላ ሀገሪቱ በትምህርት ተሰጥቶ የስራ ቋንቋ አይሆንም፡፡ አማርኛም በታሪክ አጋጣሚ የመጣ ቋንቋ ነው፡፡ በግድ እና በልዩ ጥቅም ሳይሆን ለምን በትምህርት አናስፋፋውም፡፡

==============================

“አዲስ አበባ ላይ የመወሰን መብቱ የአዲስ አበባ ህዝብ ነው”

ኢ/ር ይልቃል ጌትነት (ፖለቲከኛ)

በመሰረቱ የእኛ ህገ መንግስት የኢትዮጵያ የስልጣን ባለቤት የሚላቸው ዜጎችን ሳይሆን ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦችን ነው፡፡ አንድ ዜጋ በራሱ ስልጣን የለውም ማለት ነው፡፡ በአንድነት ከሚያስተሳስሩን ይልቅ ልዩነት ላይ ያተኮረ ነው፤ ህገ መንግስቱ ራሱ፡፡ ከዚያ በመቀጠል ደግሞ በአንድ ሀገር ውስጥ ልዩ ጥቅም ማለት የተዛባ አመለካከት ነው፡፡ ከባዕድነት የሚመነጭ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ወጣቶች ከአራቱም የሀገሪቱ አቅጣጫ ባድመ ላይ ሄደው ሲሰዉ ሀገራችን ለሁላችንም እኩል ናት፤ አባቶቻችን ጠብቀው ያዩዋት፣ ሀዘንም መከራንም እኩል የምንካፈልባት ናት ብለው ነው። ይሄ ልዩ ጥቅም ደግሞ ከዚህ አስተሳሰብ የራቀ፣ ከባዕድነት የሚመነጭ ነው፡፡ በዚህ ልኬት ከሄድን ደግሞ የአባይ ምንጭ ጎጃም ነው፣ የህዳሴው ግድብ ደግሞ ቤኒሻንጉል ነው፡፡ ስለዚህ የጎጃም ህዝብ፤ የአባይ ምንጭ ባለቤት በመሆኔ ልዩ ጥቅም ይገባኛል፣ ቤኒሻንጉል፤ ግድቡ የኔ መሬት ላይ ስላረፈ ልዩ ጥቅም ይገባኛል ሊባል ነው፡፡ ስለዚህ ይሄ አስተሳሰብ ራሱ ከመሰረቱ የተሳሳተ ነው፡፡ ዜጎችን በአንድነት በማስተሳሰር፤ ልዩነትን በማክበር፣ የጋራ የሚያደርጉንን ነገር ማዳበር ሲገባ፣ ይሄ ግን በትኖ እንደገና መሰብሰብ አይነት አስተሳሰብ ስላለው በኔ እይታ መሰረታዊ ስህተት ያለው ነው፡፡
ተረቀቀ የተባለው አዋጅም ከህገ መንግስቱ አንፃርም ቢሆን መሰረት የሌለው ነው፡፡ ለምሳሌ ከአዲስ አበባ ለሚፈናቀሉ የኦሮሞ” አርሶ አደሮች ካሳ ይከፈላል ይላል፡፡ ይሄን ማለት ለምን አስፈለገ። በኦሮሚያ ውስጥ ኦሮሞ ያልሆኑም ይኖራሉ፡፡ በክልሉ በሚወጣው ህግ በጋራ ይጠቀማሉ፤ የሚጎዱም ከሆነ በጋራ ይጎዳሉ፡፡ ታዲያ እንዲህ አይነት ከፋፋይ ነገር ለምን ያስፈልጋል፡፡ ቢያንስ በአዲስ አበባ ዙሪያ የሚኖሩ አርሶ አደሮች በሙሉ ማለት ምን ይከብዳል? የኦሮሞ አርሶ አደሮች ብሎ መለየቱ ለምን አስፈለገ? የሌላ ብሄር ተወላጅ በአካባቢው ቢኖር ይሄ አዋጅ አይመለከተውም ማለት ነው፡፡ ይሄ በዚህ ረቂቅ ውስጥ ያየሁት አንደኛው ችግር ነው፡፡
ሁለተኛ አዲስ አበባ በሽግግር መንግስቱ ጊዜ ራሱን የቻለ ክልል ነበር፡፡ በኋላ ደግሞ በቻርተሩ መሰረት ራሱን በራሱ የሚያስተዳድር ሆነ። ይሄ ከሆነ ደግሞ በህገ መንግስቱ ላይ በግልፅ እንደተቀመጠው፤ የራሳቸውን የሥራ ቋንቋ የሚወስኑት የሉአላዊ ስልጣን ባለቤቶቹ ክልሎቹ ራሳቸው ናቸው፡፡ አሁን የቀረበው ረቂቅ አዋጅ ደግሞ የአዲስ አበባ የሥራ ቋንቋ ከአማርኛ ጎን ለጎን ኦሮሚኛ ይሆናል ይላል። በህገ መንግስቱ መሰረት፣ ይሄን መምረጥ ያለበት ማን ነው?
አዲስ አበባ ተወልዶ ያደገ ሰው ደግሞ መግባቢያው አማርኛ ነው፡፡ ኦሮሚኛ መናገር ስለማይችሉ ከስራ ይገለላሉ ማለት ነው፡፡ ይሄ የዜጎችን መስተጋብር የሚንድና የከፋፋይነት ባህሪ ያለው አዋጅ ነው፡፡ ህገ መንግስቱም ይሄን ነገር አይደግፈውም፤ ምክንያቱም አዲስ አበባ ራሱን በራሱ የሚያስተዳድር፣ ተጠሪነቱ ለፌደራል መንግስት መሆኑ በግልፅ ተቀምጧል፡፡
ሃውልትን ለመሳሰሉት ቦታ መርጦ ማስቀመጥ ያለበት የግዛቲቱ አስተዳዳሪ፣ የአዲስ አበባ አስተዳደር ነው፡፡ ሌላው እንዴት ነው ስልጣን የሚኖረው? ከህግም ከሞራልም አንፃር አዋጁ፤ ከፋፋይና ህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን የሚጎዳ፣ የሀገርንም እድገት የሚፈታተን ነው፡፡ አዲስ አበባ ላይ የመወሰን መብቱ የአዲስ አበባ ህዝብ ነው፡፡   

===================================


“በቻርተር በተቋቋመ ከተማ ውስጥ አንዱን ለይቶ ተጠቃሚ ማድረግ ተገቢ አይደለም”

አቶ ክቡር ገና (በቢዝን መሪ)
የኦሮሚያ ዋና ከተማ ቀደም ሲል አዳማ ነበር፤ በኋላ በ1997 ወደ አዲስ አበባ መጣ፡፡ ይሄ ማለት አንድ ከተማ ለሁለት አካላት ዋና ከተማነት ያገለግላል ማለት ነው፡፡ አስተናጋጁ ደግሞ የኦሮሚያ ክልል ሆነ ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም የአዲስ አበባ አስተዳደር እንደ ጭሰኛ ነው የሆነው፡፡ አስተዳደሩ መሬት ይኖረዋል፣ ህንፃዎች ይኖሩታል፤ በሌላ በኩል ግን ግዛቱ የኦሮሚያ ነው፡፡ ይሄ ነው ዋናው ነጥብ። የልዩ ጥቅም ጉዳይን ስናነሳም፣ ከእንዲህ ያለው ትስስሮሽ ምን ልዩ ጥቅም ይጠየቃል? እንድንል ያስገድደናል። ልዩ ጥቅም ሊገባ ይችል የነበረው አዲስ አበባ ራሱን የቻለ ነፃ ከተማ ቢሆን ኖሮ ነው፡፡ ማለትም ሌላ ከተማ ባይደረብበት ነበር፡፡ ይሄን ስል ከተማዋ ለሁለት መንግስታት መቀመጫ መሆኗን ከግንዛቤ በማስገባት ነው፡፡ አዲስ አበባ ራሱን የቻለ ነፃ ከተማ ቢሆን ኖሮ ልዩ ጥቅም መነሳቱ ላይደንቅ ይችላል፡፡
ህገ መንግስቱ የፌደራል መንግስቱ ዋና ከተማ አዲስ አበባ ነው ሲል እና ኦሮሚያ ደግሞ መቀመጫውን አዲስ አበባ ሳይሆን አዳማ እንዳደረገ ቢቀጥል ነበር የልዩ ጥቅም ጉዳይ ሊነሳ የሚገባው። አሁን ግን አዲስ አበባ የኦሮሚያ ዋና ከተማ በሆነችበት ልዩ ጥቅም እንዴት ሊታሰብ ይችላል? የቋንቋ ጉዳይም ኦሮሚያ በግዛቴ ውስጥ የሥራ ቋንቋዬ ኦሮሚያ ነው ካለ አዲስ አበባንም ይጨምር ነበር ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ዋና ከተማውን ወይም መቀመጫውን አዲስ አበባ ስላደረገና ግዛቴ ነች ስላለ፡፡ በከተማው ቋንቋው ስራ ላይ ሳይውል ይቆይ እንጂ ይሄ አዋጁ ሳይወጣ በፊትም ኦሮሚያ ቋንቋውን በስራ ቋንቋነት እንዲጠቀምበት ተፈቅዶለት ነበር፡፡ ኦሮሚያ ቋንቋውን በአስተዳደሩ ውስጥ መጠቀም ይችል ነበር፡፡ እንግዲህ የልዩ ጥቅም ጉዳይ የኦሮሚያ ክልል ዋና መቀመጫውን ከአዳማ ቀይሮ አዲስ አበባ ሲያደርግ ያለቀ ጉዳይ ይመስለኛል፡፡
አዲስ አበባ በቻርተር የተቋቋመች ከተማ ነች። የሀገሪቱ ዋና ከተማ ነች፡፡ ዋና ከተማ ስትሆን ደግሞ ከሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚመጣ ሁሉ የሚስተናገድባት ነች፡፡ ይህ በሆነበት ሁኔታ በዚያ ከተማ ውስጥ የተለየ ጥቅም ሊያገኝ የሚችል አካል ሊኖር አይገባም፡፡ ይሄ ህዝብን መለያየት ነው፡፡ በቻርተር በተቋቋመ ከተማ ውስጥ አንዱን ለይቶ ተጠቃሚ ማድረግ ለሙስና በር ይከፍታል፣ ከአንድነት ይልቅ መከፋፈልን ያመጣል፡፡
እኛ ሀገር የፌደራል ጉዳይ ሚኒስቴር የሚባል አለ፡፡ ሚኒስቴር መ/ቤቱ በምን ላይ እንደሚሰራ አይታወቅም፡፡ ህዝብን በማቀራረብ ላይ ነው? በመሬት ጉዳይ ላይ እየሰራ ነው ወይስ ትምህርት በመስጠት ላይ ነው? ይሄ ለኔ ግልፅ አይደለም፡፡ የፌደራል ስርአት ውስጥ በጣም አስቸጋሪ ሁኔታዎች ይኖራሉ፡፡ በአንድ በኩል ማዕከላዊ መንግስቱ ስልጣኑን ማጠናከር ይፈልጋል፤ በሌላ በኩል ደግሞ ክልሎቹ በራሳቸው መንገድ የራሳቸውን ስልጣን ማጠናከር ይፈልጋሉ፡፡ እንግዲህ ዋናው ቁምነገር በዚህ መሃል ያለውን ሚዛን መፈለግ ነው፡፡ ለምሳሌ ኦሮሚያ ከሀገሪቱ ሰፊው ግዛት ነው፤በርካታ ክልሎች ያዋስኑታል፡፡ ስለዚህ ክልሉ ከሌሎች ክልሎች የተለዩ ጥያቄዎች ቢኖሩት ፌደራል መንግስቱ ያንን የመንከባከብ ግዴታም ይኖርበታል ባይ ነኝ፡፡
በእኛ ሀገር ተሞክሮ አሁንም ድረስ የሚታየን የማዕከላዊ መንግስት ጥንካሬ ብቻ ነው፡፡ አሁን ግን የክልል መንግስታት ጥንካሬ ሊኖር እንደሚችል ማሰብ መቻል አለብን፡፡ ይሄ ጥንካሬ ሲመጣ የሚጠይቁት ጥያቄ ለፌደራል መንግስቱ አስቸጋሪ ሊሆን ይችላል፡፡ ሌላው እዚህ ጋ መነሳት ያለበት ጉዳይ፣ እንዲህ አይነት ጉዳዮች ህዝብ ነው ሊወስንባቸው የሚገባው። የህዝብ ውይይት ተካሂዶ ሊረቀቅ የሚገባው እንጂ ዝም ብሎ ተፅፎ ወደ ህዝቡ ማውረድ ተገቢ አይደለም፡፡

================================

“ያለውን ግፊት እንዳለ ከተቀበልነው የወደፊታችን አስጊ ይሆናል”
አቶ ኢየሱስወርቅ ዛፉ (የቢዝነስ መሪ)

እኔ በውይይት በጣም አምናለሁ፡፡ በአሁኑ ሰዓት የፌደራል ስርአትን ተቀብለን እየሄድን ነው ያለነው። ይሄን ተቀብለን ስንሄድ አንድ ላይ ሆነን አንድ ህገ መንግስት እንዳፀናን፣ አንድ የኢኮኖሚ ማህበረሰብ እንገነባለን ብለን እየሄድን እንደሆነ ሁሉ፣ ፌደራል ስርአታችን አንድ መቀመጫ ያስፈልገዋል፤ሰማይ ላይ ተቀምጦ መስራት አይችልም፡፡ አሁን ያለው ግፊት ወደ ኋላ ተመልሰን እንደ መሄድ ይመስላል። በኦሮሚያ ብቻ ሳይሆን በአማራ ክልልም እስከ 8ኛ ክፍል ተማሪዎች በአፍ መፍቻ ቋንቋ በአማርኛ ብቻ ይማሩ የሚል ነው የምሰማው፡፡ ይሄ ሁሉ ለዘለቄታው ልንገነባው ለምናስበው፣አንድ የኢኮኖሚ ማህበረሰብ ግባችን አይወስደንም፡፡
 ፌደራል መንግስት ካቋቋምን፤ አንድ የፌደራል መንግስቱ መቀመጫ የሆነ፣ ማንም ሌላ ክልል የማያዝበት፣ ፌደራል መንግስቱ ብቻ የሚያዝበት መኖር አለበት፡፡ የዚህ ስርአት መቀመጫ ደግሞ በህገ መንግስት እንደተቀመጠው አዲስ አበባ ናት። ይሄ ማለት አንድ ክልል ብቻውን የሚቆጣጠራት አዲስ አበባ ሳትሆን የሁሉም ኢትዮጵያዊ ነች፡፡ ይህቺ ሀገር ደግሞ አብረን ሆነን እንጂ ብቻ ለብቻ ሆነን አይደለም ወደፊት ልናራምዳት የምንችለው። ለዚህ ደግሞ በፌደራል ስርአት እንተዳደራለን ግን አንድ ኢትዮጵያ ሆነን እንቀጥላለን ብለን ነው የተስማማነው፡፡ ይህ እስከሆነ ድረስ አንድ የፌደራል መቀመጫ፣ የሁሉም የሆነች፣ አንዱ ለብቻው የማያዝባት ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡
አንድ አጋጣሚ እዚህ ላይ ልጥቀስ፡፡ ናይጄሪያ ከሌጎስ ወደ አቡጃ ዋና ስማቸውን ሲቀይሩ እዚያ ነበርኩ፡፡ በወቅቱ ከበርካታ ክልሎች መሬት አዋጥተው ነው አንድ አቡጃ የምትባል ግዛት የፈጠሩት፡፡ የማንም ብሄር መኖርያ ይሁን ብቻ አንድ የተወሰነ ቦታ ተቆርሶ ነው ከተማው የተመሰረተው። የአዲስ አበባም እንዲሁ ነው መታሰብ ያለበት፡፡ የፌደራል መቀመጫ ነች ብለን መቀበል አለብን፡፡ አንዱ ከሌላው የበለጠ ወይም የተሻለ ኢትዮጵያዊ መሆን አይችልም፡፡
ልዩ ጥቅም ሲባል ምን ማለት ነው? መቼም አንደኛችን ከሌላችን የበለጥን ወይም የተሻልን ኢትዮጵያዊ አይደለንም፡፡ ለዚህች ሀገር እኩል ነን። ጥሩ ነገር ለመስጠትም ቢሆን አድሎአዊ እስከሆነ ድረስ ጥሩ አይደለም፡፡ ህገ መንግስታችን ተረቅቆ ተግባራዊ ከመደረጉ በፊት ስለ ኢትዮጵያ የወደፊት እጣ ፈንታ ለመነጋገር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፣ ወ/ሮ ገነት ዘውዴ የተካተቱበት 5 ልዑካን ሌጎስ መጥተው አነጋግረውኝ ነበር፡፡ በወቅቱ ስለ ሀገራችን ሁኔታ ስንነጋገር ብዙ ነገሮች ነገሩኝ፡፡ አንዳንድ ብሄሮች የራሳችንን ፋንታ ከኢትዮጵያ ቆርጠን እንወስዳለን ብለው የተነሱ አሉ፤ ይሄ እንዳይሆን እየሞከርን ነው ብለው አስረዱኝ፡፡
በወቅቱ ክልሎችን ፈጠራችሁ፤ ድንበር ወሰናችሁ፤ ይሄን እንዴት አደረጋችሁ? ይሄ ሊደረግ የሚገባው በሽግግር መንግስት ሳይሆን በህዝበ ውሳኔ ነበር፤ ይሄን ማድረጋችሁ የሽግግር መንግስት ላይ ሆናችሁ ስር ነቀል ለውጥ ነው፤ ይሄ ትክክል አይደለም ብያቸው ነበር፡፡ በሌላ በኩል የብሄር ፌደራሊዝም ጥንቃቄ የሚያስፈልገው ጉዳይ ነው። እንደው የግድ ከሆነ የሚያቀራርቡንና የሚያገናኙን እሴቶች እንዳይዘነጉ እባካችሁን ተጠንቀቁ፡፡ ብሄር ላይ ብቻ ካተኮርን የተዳፈነ እሳት ሆኖ ነገ ያቃጥለናል ብያቸው ነበር፡፡ አሁን አንዳንድ የማየው ነገር ያን ጊዜ ኢትዮጵያ ልትቆራረጥ ነው በሚል ፍራቻ አንዳንድ ሊደረጉ የማይገባቸው ጉዳዮች ለጊዜው በሚል በመደረጋቸው የመጣ ነው። ይሄ የልዩ ጥቅም ጉዳይም አንዱ ይመስለኛል፡፡
እኔ አስብ የነበረው አብረን በቆየን ቁጥር ተነጋግረን፣ ትክክለኛው ይሄ ነው፤ ያኔ በነበረው ሁኔታ ያስፈልግ ነበር፤ አሁን ግን ያስፈልገናል ወይ ብለን የበሰለ ውይይት አድርገን የበለጠ መቀራረብ ይመጣል የሚል ነበር፡፡ አሁን ግን ሳየው ሁኔታው አስፈሪ ነው። አሁን ያለውን ግፊት እንዳለ እንቀበለው ብንል በእርግጥም የወደፊት ሁኔታችን አስፈሪ ይሆናል የሚል ስጋት አለኝ፡፡
አዲስ አበባ የግድ ራሷን የቻለች የፌደራል መንግስቱ መቀመጫ መሆን አለባት፡፡ የኢትዮጵያ የወደፊት ስዕልን ማየት ከተፈለገ፣ የአንድ ወገንን ጥቅም በዚህች ከተማ ላይ ማድረጉ አስፈላጊ አይመስለኝም። እንዲህ አይነቱ ሁኔታ ያለፉትን 26 ዓመታት ለመቀራረብ ምንም አልሰራንም እንደ ማለት ነው፡፡ ፖለቲካችንም እንዲሁ ጥሬውን ቆይቷል እንደ ማለት ነው፡፡
የአዋጁ አፀዳደቅ አካሄዱ በራሱ ትክክል አይደለም። የሚኒስትሮች ምክር ቤት የማፅደቅ ስልጣን የለውም፡፡ ለህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ነው መምራት ያለበት፡፡ እኔ ሳስበው የፖለቲካ ክፍፍል በአመራሩ ላይ ያለ ያስመስላል፡፡ እንዲህ አይነቱ አለመግባባት ደግሞ ለተደራጀ ኃይል ስልጣን ማስወሰድን ነው የሚያስከትለው፡፡ በተማሪ ንቅናቄ ጊዜ የተማሪዎች መሪዎች ተሰብስበን፣ ጃንሆይ ይህቺን ሀገር ዲሞክራሲያዊ ቢያደርጉ ጥሩ ነበር፤ ካልሆነ ግን ሀገሪቱ የተደራጀ ቡድን ላይ ነው የምትወድቀው ብለን ነበር፡፡ በወቅቱም ወታደሩ ሥልጣኑን ሊነጥቅ ይችላል ብለን ነበር፤ እንዳልነውም ስልጣኑን ወታደሩ ወሰደ፡፡  የዛሬው ወታደር ህዝባዊ ነውና ከእንዲህ አይነቱ ድርጊት ይቆጠብ ይሆናል። ነገር ግን ይሄ እንዳይሆን መመኘትና አምላክንም መማፀን ያስፈልጋል፡፡ በእውነቱ በአሁኑ ሰዓት በአደገኛ ሁኔታ ውስጥ ነው ያለነው፡፡     

“መንግስት፤ አዳዲስ መጫወቻ እንደሚያምረው ሕጻን አዲስ ተ ሽከርካሪ በተመረተ
ቁጥር ለመግዛት ከቋመጡ፤ በየዓመቱ መጀመርያ ላይ አዳዲስ ሞባይል፣ ኮምፒዩተርና
የቢሮ ቁሳቁስ ከሚያግበሰብሱ እንዲሁም አዲስ ሕንጻ ባለቀ ቁጥር ለመከራየት


ዜጎች በሃገራቸው ላይ ሰርቶ የመኖር መብታቸው ሕገ መንግስታዊ ጥበቃ የሚደረግለት ለይስሙላ አይደለም፡፡ መሰረታዊ ግቡ የመንግስት ድጎማን ጨምሮ ከውስጣዊም ሆነ ከውጫዊ ሃይሎች ጥገኛነትና ተመጽዋችነት ተላቀው፣ እራሳቸውንና ቤተሰባቸውን በስርዓቱ መምራት እንዲችሉ ለማድረግ ነው፡፡ ነግደውም ሆነ ጉልበታቸውን ሸጠው የሚያድሩ  ዜጎች፤ ከግብር ከፋዮች ተርታ ተሰልፈው ማህበራዊ ግዴታቸውን መወጣትና ሌሎችን መርዳት የሚገባቸው የሙሰኞችንና ጊዜ የወለዳቸውን ዘመናዊ ፊውዳሎች ቁሳዊ ፍላጎት ለማሟላት ሲባል፤ በግምትና በይሁንታ ላይ ተመስርቶ መሆን የለበትም፡፡ ግብር መክፍል የዜግነት ግዴታ የመሆኑን ያህል ሕጋዊነትንና ወጥነትን በተከተለ የግብር አከፋፈል ስርዓት እየተመሩ መሆን አለበት፡፡
በዚህ ጉዳይ ላይ መሰረታዊ የሆነውን የግለሰቦች መብት በቅድሚያ ለማስቀመጥ የፈለግኩት፤ በችርቻሮ ንግድ ላይ  የተሰማሩ የመለስተኛና አነስተኛ ግብር ከፋይ ነጋዴዎች ሰሞኑን ከገቢ ግምትና ከግብር ክፍያ ስርዓት ጋር ተያይዞ እያሰሙ ያለው እሮሮ እጅግ አሳሳቢ ሆኖ ስላገኘሁት ነው፡፡
በነጋዴው ማህበረሰብና በመንግስት መካከል ይህን ያህል ሰፊ ልዩነትና አለመግባባት መከሰቱ እውን በአንድ ሃገር ውስጥ የሚገኙና ስለ አንድ ዓይነት ጉዳይ የሚወያዩ አይመስልም፡፡ ነጋዴዎች፤ “የማንንም እጅ ሳናይ ከማንም ምንም ሳንጠብቅ ቀኑን ሙሉ እግራችን እስኪንቀጠቀጥ ድረስ ሱቅ በር ላይ ቆመን  ከእጅ ወደ አፍ በሆነ ገቢ የእለት ጉርሳችንን አሸንፈን ቤተሰብ በደጎምን፤ ሰምተንና አይተን የማናውቀውን የሚሊዮን ብር ባለዕዳ የሚያደርገን መንግስት ምን ያህል ቢጠላን ነው? “  የሚል ጥያቄ ያነሳሉ፡፡
ቀሪዎቹ ደግሞ “ከኛ በሚሰበሰብ ግብር የሚተዳደሩ ሹመኞች በየሚዲያው እየቀረቡ ትንታኔ ሲሰጡ፣ ነጋዴውን ማህበረሰብ እንደ አጭበርባሪ፣ ግብር የሚሰውሩ ሕገ ወጦችና በጥቅሉ  እንደ ተጠርጣሪ ዜጋ የሚፈርጁን ምን ሕጋዊ መሰረት ይዘው ነው? በዚህም ምክንያት አሁን አሁን ነጋዴ መባል ሌባ ከመባል ያልተናነሰ ገጽታ እንዲኖረንና እንድናፍር አድርገውናል” የሚል ቅሬታ ይሰነዝራሉ።
ዞር ዞር ብዬ ለመታዘብ እንደሞከርኩት፤ አብዛኞቹ  አነስተኛ ግብር ከፋይ ነጋዴዎች በመቶ ሺህ ብር የሚቆጠር ወረት ይዘው የሚቸረችሩ ናቸው። ይህንን ወረት ስንት ጊዜ ደጋግመው ቢሸጡት አመታዊ ገቢያቸው ሁለት ሚሊዮን ብር ሊደርስ እንደሚችል የሚያስረዳኝ ማግኘት አልቻልኩም! የሂሳብ ሙያ ትምህርቴ  ቢሆንም አዕምሮዬ አውጥቶ አውርዶ ስሌት መፍጠር አልቻለም፡፡ የሚያስደንቀው ነገር ደግሞ በተሰጣቸው የገቢ ግምት ማሳወቂያ ደብዳቤ ላይ፤ ‹‹የንግድ ድርጅትህ/ሽ ገቢ ተገምቶ በዓመት ይህንን ያህል ገቢ እንዳለህ/ሽ ተረጋግጦብሃል›› በማለት ግምትና ማረጋገጥን መሳ ለመሳ በመፋረጃነት ማቅረባቸው ነው፡፡
አንጀታቸው የቆሰለ በርካታ ዜጎች እንደተበራከቱ ከየመገናኛ ብዙኃኑ ላይ ለመረዳት ችያለሁ፡፡ መነሻቸው ደግሞ ሌላ አይደለም፤ ወጥነትና ስርዓት ባልተከተለ መንገድ አምስት ደቂቃ በማይሞላ ጉብኝት፤ አንዳችም ሙያዊ ትንታኔና እውቀት ሳይታከልበት፣ የዓመት ሽያጭህ/ሽ አንድ ሚሊዮን ወይም ሁለት ሚሊዮን ነው መባሉ ነው፡፡ ይሄ በእርግጥም ግራ ከማጋባቱም በላይ አንጀት እርር ድብን ያደርጋል፡፡ ገፋ ሲልም ከድንጋጤ የተነሳ ለተለያየ  በሽታ የተዳረገውን  ቤቱ ይቁጠረው ከማለት ውጭ መልስ ሊገኝለት አይችልም፡፡
‹‹ተጠርጣሪ ዜጎች››
 ኢህአዴጋውያንን ለጫካ አመጽ ከዳረጋቸው የደርግ ስርዓት ኢ-ዴሞክራሲያዊ መገለጫዎች መካከል፤ ዜጎችን በጅምላ የመጠርጠርና የመፈረጅ አባዜ አንዱ ነበር፡፡ ዜጎችን በጅምላ የመጠርጠርና የመፈረጅ አባዜ ለደርግ ሹመኞች በሕግ የተፈቀደ መብት ነበር፡፡  ደርጎች፤ ከአብዮት ጥበቃ ጀምሮ እስከ ሚኒስትሮቹ ድረስ ጸጉሩን ያጎፈረን ሁላ ፀረ-አብዮተኛ ነው በማለት በጅምላ ፈርጀው፣  ያለ በቂ ማስረጃና ማጣራት  ማሰር፤ በድብደባ አካለ ጎዶሎ ማድረግና መግደል… ጥያቄ የሚነሳበትና ሕግ ፊት የሚያቀርብ ጉዳይ አልነበረም፡፡ በዚህ መንገድ ቁጥራቸውን ለመገመት የሚያዳግቱ  ዜጎች ጥሩ በመልበሳቸው፤ የተደላደለ ቁመናና ያልተጎሳቆለ ገጽታ ስለነበራቸው ብቻ ‹‹በዝባዥና ፊውዳል›› በሚል ጥቅል ፍረጃ በህዝብ ፊት ተዋርደው ከማህበረሰቡ እንዲገለሉ ተደርገዋል፡፡ ሰብእናቸው ተዋርዶ የበረታባቸውም እጅግ ለሚዘገንን ኢ-ሰብአዊ  እስርና እንግልት፣ አልፎ ተርፎ ሞት ተዳርገዋል፡፡
ይህ ዘመን ፈጽሞ እንዳይደገም አገር ተማምሎ ሕገ መንግስት ባጸደቅን 25 ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በፖለቲካ አመለካከታቸው ሳይሆን ሰርቶ ለመብላትና ኑሮአቸውን ለማሸነፍ ደፋ ቀና የሚሉ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ነጋዴዎች በጅምላ ሲፈረጁ፤ ሲጠረጠሩ ከማየት አልፈን ተርፈን፤ ይሄው  የተዛባና ጤናማ ያልሆነ አመለካከት እንደ መብት ተቆጥሮ፣ ያለአንዳች ይሉኝታና መታቀብ በየአደባባዩና በሕዝብ መገናኛ ብዙሃን ሳይቀር በስፋት ሲነገር ለማዳመጥ በቅተናል፡፡ ሰሞኑን ከገቢ ግምት ጋር ተያይዞ፣ ነጋዴዎች በሕገ መንግስቱ ላይ የሰፈረ መብታቸውን ተጠቅመው ተቃውሟቸውን እንዳያሰሙ ለማድረግና ቀድሞ አፍ ለማዘጋት  ሲባል፣ ግብር በመሰወርና ገቢ በማሳነስ ጅምላ ተጠርጣሪነት ሲፈረጁ በስፋት አድምጠናል፡፡
ሕገ መንግስቱ ዜጎች ኢ-ሰብአዊ ለሆነና ሰብእናቸውን ለሚነካ ድርጊት አይጋለጡም ቢልም፣ ነጋዴውን ማህበረሰብ በጅምላ መጠርጠርና ከጥርጣሬ ተነስቶ ሰብእናውን የሚነካ ሃሳብ መሰንዘር ወይም ከጥርጣሬ ተነስቶ ሰርቶ የመኖር መብቱን የሚፈታተኑ ሕጎችና ድንጋጌዎችን ማውጣት ላለፉት በርካታ ዓመታት የተለመደ ጉዳይ ነው፡፡
የአዲስ አበባ ነጋዴዎች በተለይ ደግሞ በመለስተኛና አነስተኛ ንግድ ላይ የተሰማሩ ዜጎች፣ ባለፉት አስር ዓመታት ውስጥ ለበርካታ ጊዜ ገቢ በመሰወርና ግብር በማሳነስ እየተጠረጠሩ ዓመታዊ ገቢያቸውና የሚከፍሉት ግብር በተደጋጋሚ ተከልሷል፡፡ በዚህም ምክንያት ተረጋግተው ስራቸውን ለማከናወንና የንግድ ሥራቸውን ለማስፋፋትም ሆነ የሚጠበቅባቸውን የግብር ግዴታ ለመወጣት አልታደሉም፡፡ ህይወታቸውም እንደ ቆቅ የስጋት ነው፡፡ ዘንድሮ የማይጠበቅ  ግብር ይጣልብኛል በሚል ስጋትና በድብብቆሽ ተጠምደው ጊዜያቸውን እየገፉ እንደከረሙ ግልጽ ነው፡፡  የዘንድሮው ፈተና ደግሞ ከፈተናም የከበደ ፈተና!
‹‹ሁለተኛ ዜግነት››
በበርካታ አገራት እጃቸውን አጣምረው ከመንግስት የስራ ዕድል የማይጠብቁ፣ በራሳቸው ጥቂት ጥሪት፣ ጉልበታቸውንና ጊዜያቸውን ተጠቅመው፣ ኑሮአቸውን የሚያሸንፉ ዜጎች ከተደራራቢ ግብር ነጻ እንዲሆኑ ይደረጋሉ። በተቃራኒው ለመሰረተ ልማት፣ ለሃገር ደህንነት የሚውል የግብር ከፋዩን ገንዘብ እጃቸውን አጣምረው የሚጠብቁ ዜጎች ደግሞ ድርጊታቸው የሚበረታታ ሳይሆን የሚነወር ነው፡፡ በአብዛኛዎቹ ሃገራት የመንግስት ድጋፍ የሚደረግላቸው ዜጎች፤ በልዩ ድጋፍ ውስጥ የሚታቀፉ  በተለይ መስራት የማይችሉ፣ ቤተሰብ አልባ የሆኑ ሕጻናት ወይም ሀገራቸውን አገልግለው ጧሪ በማጣታቸው የተቸገሩ አረጋውያንና የመሳሰሉት ናቸው፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ግን የሚሰራው በተቃራኒው ነው፡፡ ሃገር መለወጥ የሚጠበቅባቸውና መስራት የሚችሉ ዜጎች፤ መሬትና ገበያ በነጻ ተመቻችቶላቸው፣ መንገድ ተለቆ ግብር ሳይከፍሉ ይነግዳሉ፡፡ በራሳቸው ጥሪት ድርጅት ከፍተው፣ ኑሮአቸውን ለማሸነፍ የሚታገሉ ዜጎች ግን ከመጠርጠር ጀምሮ የሌሎችን ሕይወት ለመለወጥና “ሚሊዬነር” ለማድረግ  የማይሞላ ኮሮጆ እንዲሞሉ ይጠበቅባቸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሕገ መንግስት ስለ ዜጎች እኩልነት በሰፊው ይዘረዝራል፡፡ በአጠቃላይ ግንዛቤ ደረጃ ዜጎች በተፈጥሮም ሆነ በሕግ ፊት እኩል መሆናቸው ይታወቃል፡፡
ማንኛውም ዜጋ ከፍላጎቱ ውጭ የሌሎችን ሕይወት ለመለወጥም ሆነ ለመደጎም  ሲባል በቀጥተኛም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ በጉልበቱና በላቡ ያፈራውን ሃብትና ጥሪት እንዲያጋራና እንዲያካፍል ሊገደድ አይገባውም፡፡ በግብር መልክ የሚሰበሰብ ገንዘብም ቢሆን ለዜጎች የጋራ ጥቅም የሚውሉ መሰረተ ልማቶችን ለማሳካትና  የሁሉንም ዜጎች ደሕንነት ለማስጠበቅ፣ የሃገርን ሉአላዊነት ለማስከበር ከመዋል ውጭ የማንንም ሕይወት ለመደጎም መዋል የለበትም፡፡ በዚህ መንገድ የሚደረግ ጉዞ ደግሞ ተያይዞ የመውደቅና የዜሮ ድምር ውጤት ከመሆን አያልፍም፡፡
የዜጎች እኩልነት የሚረጋገጠው በተፈጥሮና በሕግ ፊት እንጂ ክህሎቱን፣ ጥሪቱን፣ ጊዜና ጉልበቱን አፍስሶ ከሚሰራው ዜጋ ላይ በግብር ስም ሀብት እየቀነሱ፣ ስራ የለም በሚል እጃቸውን አጣምረው ለተቀመጡና በግብር ከፋዩ ሀብት ተሽከርካሪ፣ ሕንጻና የቢሮ ቁሳቁስ ለሚያማርጡ ሙሰኞችና አባካኞች ካዝናውን ምቹ በማድረግ ሊሆን አይገባም፡፡  ይህ ከሆነ ደግሞ ስርዓቱ ዛሬም እንደ ቀደምት ስርዓቶች ሁላ አንዱ ሳይሰራ ሕይወቱን የሚያደላድልበትና ቀሪው ደግሞ እንደ ሁለተኛ ዜጋ  ተቆጥሮ፣ በዘመናዊ አገልጋይነት የላብና የድካሙን ዋጋ ከሚገፈግፍበት ከፊውዳሎች ስርዓት የሚሻል አይሆንም፡፡
ለብልጽግና እና ለእድገት የበቃ ስርዓት ያላቸው ሀገራት፤ ዜጎቻቸው በእውቀታቸውና በላባቸው ያፈሩትን ሃብት በቀጥተኛም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ለሌሎች እንዲያካፍሉ በተገደዱባቸው ሀገራት ሳይሆን የሰዎች ላብና ድካም ተገቢውን ዋጋና ክብር ባገኘባቸው ሃገራት እንደሆነ ታሪክን መለስ ብሎ ማጤን ያሻል፡፡ መንግስት ሀገራዊ ሃብቱን አቀራምቶና ተቀራምቶ፣ ሁሉንም ዜሮ በማስገባት ተያይዞ ላለመውደቅ፣ ዜጎች ሁላ እኩል በጉልበታቸው፣ በእውቀታቸውና በላባቸው ማደርን የሚያስገድዳቸው የግብር ስርዓት መዘርጋት አለበት።
የማይሞላ ኮሮጆ ሌላ ገጽታ
ዜጎች የሚከፍሉት ግብር ተገቢው ጥበቃ እየተደረገለት እንደሆነ፣ አላግባብ እንደማይባክን፣ ለሙስና እንዳልተጋለጠ አልፎ ተርፎም ለምን ተግባር እንደዋለ የማወቅ ሕገ-መንግስታዊ መብት አላቸው፡፡ ይህ መብት በተከበረበት ሃገር፤ ግብር የዜግነት፣ የሞራልም ሆነ የሕግ ግዴታ ነው፡፡ የሕዝብ ሀብት ለዘረፋ፣ ለብክነት፣ ለሙስና እየተጋለጠ ባለበት ሁኔታ ከአንድ ወገን የሚነሳ ፍላጎትን ለማሟላት ሲባል ብቻ በግብር ስም የአንዱን ሃብት በተጽእኖ ለሌላው ማጋራት ፍትሃዊነት የጎደለው ተግባር ነው።
መንግስት በየዓመቱ በኦዲት ተቋሙ አማካኝነት ለተወካዮች ምክር ቤት በሚያቀርበው ሪፖርት ላይ በቢሊዮን የሚቆጠር የሕዝብ ሃብት ለከፍተኛ ብክነት፣ ሙስና እና ዘረፋ የተጋለጠ መሆኑን ሳያስደምጥ አልፎ አያውቅም፡፡ መንግስት በተለያየ ጊዜ ፓርላማ ላይ እየቀረበ “የመንግስት ሌቦች” የሚላቸውን አንዳንድ ባለሟሎች፤ ምን ያህል የመንግስት ካዝና እንደሚቦጠቡጡ በምሬት ሳይገልጽ ውሎ አድሮ አያውቅም፡፡ መንግስት ፍጆታውን በመቆጠብ ዘረፋን፣ ሙስናንና ብክነትን በመከላከል ካዝናውን መጠበቅ አቅቶት እያለ፣ ዘረፋና ሙስና የቦጠቦጠውን ካዝና ለመሙላት ሲባል፣ ዜጎች ከፍትሐዊነት በራቀ መልኩ በየዓመቱ በግምት ላይ ተመስርቶ የሚጣልን የተጋነነ ግብር መገፍገፍ የለባቸውም የሚል እምነት አለኝ፡፡
ዜጎች፤ ሕይወታቸውን ከማሸነፍ ባሻገር ጥሪት የመያዝ፣ ሃብት የማፍራት፣ ሕይወታቸውን ወደ ላቀ የአኗኗር ደረጃ የማሳደግ መብት አላቸው። ትርፋቸውን መጠነ ሰፊ የሆነ ግብርና የማያበቃ መዋጮ ሳይቀራመትባቸው፣ ጥሪታቸውን አጎልብተው በመቆጠብ፣ የቤተሰባቸውን ሕይወት የማሻሻል መብት አላቸው፡፡ ቁጠባቸውና ያፈሩት ጥሪት ለሌላ ኢንቨስትመንት ድጋፍ ሊሆንና በሚገኘው ተጨማሪ ወረት ሕይወታቸውን ሊያሻሽሉበት ይገባል፡፡ ኢንቨስትመንትም የሚያድገው በብድርና በባለቤቶች ሃብት ብቻ ሳይሆን ዜጎች ከቁጠባቸው ላይ ሼር በመግዛት በሚያደርጉት መዋጮ ጭምር መሆኑ ሊዘነጋ አይገባም፡፡
ይህ እውን እንዲሆን ደግሞ ዜጎች በሙስና ብክነትና ዝርክርክነት በሚሸረሽረው የማያልቅ የመንግስት የገንዘብ ፍላጎት ውስጥ ተጠምደው በመዳከር ሕይወታቸውን ማሻሻል እንዳያዳግታቸው መንግስት ጥንቃቄ  ማድረግ ይገባዋል፡፡ መንግስት አዲስ የመጣ ተሽከርካሪ፣ የቢሮ ቁሳቁስና ሞባይል ለሚያምራቸው ሹመኞቹ የፍላጎት ገደብ ማበጀት አለበት፡፡ ቤታቸው ውስጥ የማይደፍሩትን ድግስ፤ በሕዝብ ሃብት አዘውትረው በመደገስ፣ በግብር ከፋዩ ሃብት ቸር ለሚሆኑ ሹመኞቹ ሲባል ግብር  በየዓመቱ መጨመር ምክንያታዊነትና ፍትሐዊነት የሚጎደለው አካሄድ ነው፡፡ ለዚህ መፍትሔው ደግሞ መንግስት አስተዳደራዊ ወጭን በአግባቡና በቁጠባ መጠቀምን መርህ በማድረግ፣ ለየሹመኞቹ ምክንያታዊነትና ፍትሐዊነትን ማስተማር ብቻ ነው። የሕዝብን ሀብት ከዘረፋ በመታደግ ግብር ከፋይ ዜጎች ከከፍተኛ የግብር ጫና እና ከእለት ተእለት ስጋት እፎይ የሚሉበት ጊዜ  እውን  መሆን አለበት፡፡ ለዘረፋና ለሙስናና ለብክነት የተጋለጠና የማይሞላ ካዝና ይዞ ሕዝብ ፊት ከመቅረብ፣ ካዝናውን ጠግኖና ቀልፍ አበጅቶ፣ ዜጎችን ተስፍ ከመቁረጥና ከተመጽዋችነት አልፎ ተርፎም የሀገርና የባዕድ ጥገኛ ከመሆን መታደግ ያሻል፡፡
ግምትና ማረጋገጥ
መሳ ለመሳ እንደ መፋረጃ
አዲሱ የገቢ ግምት አሰራር ሌላው አወዛጋቢ ገጽታው ግምቱን ለመከወን የተሰማሩት ግለሰቦች ሙያዊ ብቃት ጥያቄ ላይ የወደቀ መሆኑ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ግብር በባህላዊ መንገድ መሰብሰብ ከጀመረ በርካታ ምዕተ ዓመታት ተቆጥረዋል። የግብር አሰባሰብ ስርዓቱም በሙያ እንዲታገዝ ጥረት መደረግ ከጀመረ  ቢያንስ ከግማሽ ምዕተ ዓመት በላይ ሆኖታል፡፡ ይህ እንዳለ ሆኖ ዛሬ ላይ ግን ለግምት ስራ መስክ ከወጡት ሰራተኞች አብዛኛዎቹ ስለ ንግድና ግብይት ተመክሮም ሆነ ልምድ የሌላቸው ናቸው፡፡ ገማቾቹ ቢያንስ ቢያንስ ነጋዴው ለሽያጭ ያቀረበውን ቀሳቁስ በዋጋ፣ በጥራት ደረጃ፣ በብዛት፣ በዓይነት የሚለዩ እንዲሁም የትርፍ ሕዳጉን በየስራ ዘርፉ ተንትኖ ለመረዳት የሚያስችል እውቀትና ልምድ የቀሰሙ መሆን ነበረባቸው፡፡  
በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ላይ ሆነን፣ መንግስት የግብር አሰባሰብ ስርዓታችንን በባለሙያ፣ በዘመናዊ የኮምፒዩተርና የሶፍትዌር አመዘጋገብ ስርዓት እንዲታገዝ በማድረግ  ወጥነትና ቀጣይነት ያለው የግብር አሰባሰብ ዘይቤ ተግባራዊ መድረግ ሲገባው፤ ዛሬም ላይ ሆነን ነጋዴውን ከቀቢጸ ተስፋ ለመታደግ የሚያስችል በደመ-ነብስ ከሚደረግ የግምት አሰራር መውጣት አልተቻለም፡፡ የመንግስት የገንዘብ ፍላጎትና ወጭ ባደገ ቁጥር አስቀድሞ በመቶ ሺ የሚቆጠሩ ነጋዴዎችን በተጠርጣሪነት በመፈረጅና በማሸማቀቅ፣ እንደ ቁም ከብት ንግድ  የአቦሰጡኝ ግብር መጣል በምንገኝበት ዘመን አስተዛዛቢ ድርጊት ነው፡፡  
እጅግ የሚያስደንቀው ጉዳይ ደግሞ በአንድ ህንጻ ላይ ያሉ የሕጻንም ሆነ የሴት ወይም ወንድ ልብስ አሊያም አንደኛና ወይም ሁለተኛ አሊያም ሶስተኛ ይገኙ አሊያም ሕንጻው አስፋልት ዳር ይገኝ መንደር ውስጥ ገማቾቹ  ዓመታዊ የሽያጭ ገቢ የሚገምቱት በአብዛኛው እኩል ነው፡፡ ነገሩን እጀግ አስቂኝ የሚያደርገው ደግሞ በየስማቸው የሚሰጣቸው ደብዳቤ ይህንኑ ሲያትት በዚህ ቀን በተደረገው ግምት፣ ‹‹የቀን ገቢህ ይህንን ያህል ብር መሆኑ ተረጋግጧል” የሚል መሆኑ ነው፡፡ መገመትና ማረጋገጥ መሳ ለመሳ እየቀረቡ፣ የፈለጉትን ለመወሰን መፋረጃ ሆነው መቅረባቸው ከግዴለሽነት ውጭ ምን ትርጉም ሊሰጠው ይችላል፡፡
ግምት ግምት ነው፡፡ መነሻውም ሆነ መድረሻው ስሜት ነው፡፡ ማረጋገጥ ግን ከጥናትና ከምርምር የሚገኝ ውጤት ነው፡፡ ቢያንስ ቢያንስ ከግምት በኋላ ገለልተኛ ከሆነ አካል ጋር በይፋ ቢያንስ እንኳን ዘርፍ በዘርፍ ድርድር  ተደርጎ ቢሆን ኖሮ፣ ማረጋገጥም ሆነ ስምምነትን ማግኝት በተቻለ ነበር። ይህ ግን አልሆነም፡፡
ኃላፊነትን ሳይወጡ ኃላፊነትን እንዲወጡ መጠበቅ
እንደ አፍሪካ ባሉ ሃገራት ዜጎች በስልጣንና በፖለቲካ ጉዳይ መጠርጠራቸው ነውር የሌለው ድርጊት ነው፡፡ የአፍሪካ መንግስታት መቶ በመቶ መረጠን የሚሉትን ሕዝብ በስጋት መከታተል፤ ፈጽም የተባለውን አይፈጽምም ከሚል ጥርጣሬ በመነሳት መሰለል፣ ኢ-ፍትሐዊነትን እንዳይቃወም አስቀድሞ አጀንዳ በማስጣል ማሸማቀቅና እጁንና አፉን እንዲሰበሰብ ማድረግ የተለመደ በስልጣን ላይ የመቆያ ዘዴ ነው፡፡
ወደ ሃገራች ገቢና የግብር ስርዓት ስንመጣ፣ ይኸው የተለመደው የአፍሪካውያን መሪዎች ዘዴ ተግባር ላይ ሲውል በገሀድ እንመለከታለን፡፡ አነስተኛና መካከለኛ ገቢ ያለው ነጋዴ ማህበረሰብ የሚገኘው ትርፍ ከእጅ ወደ አፍ ከመሆንም በላይ የትርፉም አመጣጡ እንዲያው በዋዛ አይደለም፡፡ትርፉ የሚገኘው እለት ከእለት በሚደገር ከጦር ሜዳ ያልተናነሰ ትንቅንቅና ግብግብ ውስጥ ታልፎ ነው፡፡ ብዙ ሕገ ወጥ ድርጊት ማሸነፍ ይጠይቃል ፤ በሕግ ስም ከተሰማሩ ሕግ ከሚጥሱ ሕግ አስከባሪዎች ጀምሮ ከኮንትሮባንዲስቶች፣ ንግድ ሚኒስቴር ከማያውቃቸው የኮንትሮባንድ ልባሽና እቃ አዟሪዎች፣ የሃገሪቱ የንግድ ስርዓት ከማይገዛቸው ልዩ ድጋፍ ከሚደረግላቸውና መንገድ ተዘግቶላቸው የአካባቢን ንጽህናና ድምጽ በመበከል ከሚነግዱ ጋር ከፍተኛ ውድድር ተካሂዶ ነው፡፡
ከፍተኛ ነጋዴ የሚባሉትና የጅምላ አስመጭዎችና አከፋፋዮችም እጃቸው ረጅም ስለሆነ ተጸእኖአቸው ቀላል የሚባል አይደልም፡፡ ምሳሌ ልስጥ፡፡ ጅምላ አከፋፋዮች የሚያስገቡትን እቃ ለቸርቻሪዎች ሲሸጡ የሚቆርጡት የቫት ደረሰኝ አንደር ኢንቮይስ የሆነ ነው፡፡ በአምስት መቶ ብር የገዙትን እቃ ወደ ሃገር ውስጥ ሲያስገቡ ከጉምሩክ ሰዎች ጋር በመመሳጠር፣ ሁለት መቶ ብር እንደተገዛ አድርገው ተጨማሪ እሴት ታክሰ  ይከፍሉበታል። ቸርቻሪው ሲገዛ የሚጠየቀው የእቃው ዋጋ ግን የተገዛበት እውነተኛ ዋጋ ማለትም አምስት መቶ ሲደመር የጅምላ ነጋዴው ትርፍ ተጨምሮበት ነው። የጅምላ ነጋዴው ትርፍ እንበል ሁለት መቶ ብር ቢሆን የእቃው አጠቃላይ ዋጋ ሰባት መቶ ይሆናል ማለት ነው፡፡ ቸርቻሪው የሚከፍለው ይህንን ዋጋ ነው፡፡ ደረሰኝ የሚሰጠው ግን ተጨማሪ እሴት ታክስ በተከፈለበት ዋጋ ብር ሁለት መቶ እና የአከፋፋዩ ትርፍ ሁለት መቶ ብር ተደምሮ አራት መቶ ብር ብቻ ነው፡፡ የጅምላ ነጋዴዎቹ በጣት የሚቆጠሩና ምትክ የሌላቸው ስለሆኑ ለቸርቻሪው የሚሰጠው አማራጭ ከፈለክ ውሰድ አሊያም ተወው ነው፡፡ ሲያሻቸውም ደረሰኝ ይነፍጉታል፡፡ በዚህም ምክንያት ቸርቻሪው ተጨማሪ እሴት ታክስ ውስጥ መግባት አያዋጣውም፡፡ ለምን ? በሕገ ወጥ ደረሰኙና ቸርቻሪው በሚሸጥበት ዋጋ መካከል ያለው ያልተመዘገበ የጅምላ አከፋፋዩ ትርፍ የግብር እዳ ከፋዩ ቸርቻሪው ስለሚሆን ነው፡፡  
መንግስት በየተቋሙ ውስጥ ያሉ ሕገ ወጦችን መከላከል ያለበት ለነጋዴው ማህበረሰብ ብሎ ሳይሆን ሕጋዊ ግዴታ ስላለበት ነው፡፡ ነጋዴዎች ደግሞ አግባብ ላለው ትርፍ፣ ተገቢውን ግብር የመክፈል የሞራልና ሕጋዊ ግዴታ አለባቸው፡፡  በመንግስትም ሆነ በነጋዴዎች  ላይ ሕግ የሚጥለው ግዴታ እኩል ነው፡፡ ነጋዴው ማህበረሰብ ግብር የመክፍል ግዴታ ያለበትን ያህል ለከፈለው ግብር ተመጣጣኝ የሕግ ጥበቃና ከለላ የማግኘት መብት አለው፡፡
መንግስት ከሀገራዊ አጠቃላይ ምርት እድገት ጋር ተመጣጣኝ ገቢ ከግብሩ ለማግኘት በግምት ግብር መጨመር መፍትሔ ሊሆን አይችልም። ትክክለኛው መንገድ ለግብሩ መቀነስ  ምክንያት የሆኑ አካላት ወደ ሕጋዊ ስርዓቱ  እንዲገቡ ማድረግ ነው፡፡  የነገደና ያተረፈ ሁሉ ተገቢውን አገልግሎትና ግብር መክፍል አለበት፡፡ ከግብር ነጻ የሆነ አገልግሎት ማንም ዜጋ ማግኘት የለበትም፡፡ በሌላው ላብ፣ ጊዜና ጉልበት እራስን በተዘዋዋሪም ሆነ በቀጥተኛ መንገድ ማበልጸግ የሚሹም ከዚህ ድርጊት መታቀብ አለባቸው፡፡ ይህ ካልሆነ ደግሞ ድጋፉ ለሁሉም  ዜጋ በእኩል መስፈርት መሆን አለበት፡፡
ከላይ በዝርዝር ያቀረብኳቸው ከኮንትሮባንድ ንግድ ጀምሮ የመንገድ ላይ ግብይትና የኮንትሮባንድ አዟሪዎችን ጨምሮ የመንግስት ድጋፍ የሚደረግላቸው ነጋዴዎች፤ በግብር ስርዓቱ ውስጥ የሚካተቱበትን መንገድ መፍትሔ የመሻት ሕጋዊ ግዴታ መንግስት አለበት፡፡ በመጨረሻም የግብር መጠን እንዲቀንስ በማድረግ ሕጋዊ የሆነውን መካከለኛና አነስተኛ ነጋዴው በሕግ እይታ ውስጥ ስለሆነ ብቻ  ክፍተት እንዲሞላ የማድረግ ተጽእኖ እንዲቆም ከተፈለገ፣ በተለያየ ደረጃ ላይ የሚገኙ ከፍተኛ ነጋዴዎች፤ በሙስናና  በጥቅም በመተሳሰር የሚያሸሹትን ግብር እንዲከፍሉ ማድረግ፤ በሕግ ጥላ ስር የማይነግዱ ኮትሮባንዲስቶች ወደ ግብር ስርዓት እንዲገቡ መታገል ከመንግስት  ይጠበቅበታል፡፡
በመጨረሻም ዋናውና ወሳኙ ጉዳይ ከላይ ለመጥቀስ እንደሞከርኩት፤ መንግስት አዳዲስ መጫወቻ እንደሚያምረው ሕጻን አዲስ ተሽከርካሪ በተመረተ ቁጥር ለመግዛት ከቋመጡ፤ በየዓመቱ መጀመርያ ላይ አዳዲስ ሞባይል፣ ኮምፒዩተርና የቢሮ ቁሳቁስ ከሚያግበሰብሱ እንዲሁም አዲስ ሕንጻ ባለቀ ቁጥር ለመከራየት ከሚተጉ ሹመኞች፤ የግብር ከፋዩን ገንዘብ መታደግ አለበት፡፡ ብክነት የእድገት ጠር ስለሆነ በግብር ከፋዩ ድሃ ሕዝብ አቅም ልክ በቁጠባ መኖር የመንግስት ባህል መሆን አለበት፡፡ ሙስና  የመንግስትን ገቢ በቀጥተኛም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ የሚያዳክም ቀበኛ ነው። ድሃው ሕዝባችን ላቡን፣ ጊዜውን፣ ጉልበቱን አፍስሶ የሚያፈራው ሃብት፤ የሙሰኞች አስረሽ ምችውና ዳንኪራ ማድመቂያ መሆን የለበትም፡፡ ገቢ ሲያንስ ድሃ ይበላው  እንጂ ይገብረው አያጣም የሚለው አመለካከት ከፊውዳሊዝም ስርዓት ጋር አብሮ የተቀበረ አስተሳሰብ መሆን አለበት። ዜጎች ተመጣጣኝ ግብር የመክፈል ግዴታቸው እንደተጠበቀ ሆኖ፣ ጥሪታቸውን ለዘመናዊ ፊውዳሎች መገበራቸው መቆም አለበት፡፡   







በመምህርና ገጣሚ ብርሀነ ስላሴ ከበደ (ያዲስ ልጅ) የተሰናዱ ከ60 በላይ ግጥሞችን ያካተተው ‹‹ነፋስ
ያነሳው ጥላ›› የተሰኘ የግጥም መድበል ገበያ ላይ ዋለ፡፡የሀዋሳ ከተማ ነዋሪ በሆኑት መምህርና ገጣሚ ብርሀነ ስላሴ የተሰናዱት ግጥሞቹ፤ ከመምህርነት ህይወታቸው ከአካባቢያቸውና ከኑሮ ልምዳቸው ያገኟቸውን ሀሳቦች ወደ ግጥም ቀይረው ለአንባቢ ማድረሳቸውን በመግቢያው ላይ አስፍረዋል፡፡ በ75 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ ለአገር ውስጥ በ40 ብርና ለውጭ አገራት በ20 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡