Administrator

Administrator

ሚዳቆ የመጻሕፍት አሳታሚዎች ደርጅት ትላንት ከቀኑ 9፡00 ሰዓት ጀምሮ “የኮሪያ ዘመቻ”፣ “የአድዋ ድል” “የእነ ሳራ ዛፍ” እና “የሳራ ጥያቄ” የተባሉትን የህፃናት መፅሐፍ መስቀል አደባባይ ከቀይ ሽብር ሰማዕታት ሙዚየም ጀርባ በሚገኘው አዲስ አበበ ሙዚየም ውስጥ አስመረቀ፡፡ በዕለቱ የምረቃ ስነ ስርዓቱን መድረክ ደራሲ፣ ዳይሬክተርና ተዋናይት አዜብ ወርቁ የመራች ሲሆን ደራሲ እንዳለጌታ ከበደም በእንግድነት ተገኝቶ መፅሐፍቱን መመረቁ ታውቋል፡፡ በምረቃ ስነ ስርዓቱ ላይ ፀሐፍት፣ ሰዓሊዎች፣ አርታኢዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመው እንደነበር ሚዳቆ አሳታሚዎች ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡

 በአርቲስት ዓለምፀሐይ ወዳጆና በሙያ ባልደረቦቿ የሚመራውና መቀመጫውን አሜሪካ ያደረገው ዓመታዊ የኪነ ጥበብ ምሽት የፊታችን ሐሙስ ከቀኑ 10፡30 ጀምሮ በአክሱም ሆቴል ይካሄዳል፡፡
በዕለቱ የተለያዩ ግጥሞችች፣ ወጎች፣ መነባንብ፣ በአርቲስት ታምሩ ንጉሴ የሚቀርብ የክራር ሙዚቃና ሌሎችም የኪነ ጥበብ ድግሶች ይቀርባሉ፡፡
የኢትዮጵያን ኪነ ጥበብ ለማሳደግና ለወጣት የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች መድረክ ለመፍጠር ታልሞ በየዓመቱ በሚዘጋጀው በዚህ ምሽት ላይ ምልዕቲ ኪሮስ፣ ወሰን ሰገድ ገ/ኪዳን፣ በላይ በቀለ ወያ፣ ሰለሞን ሞገስና ሌሎችም ስራዎቻቸውን ያቀርባሉ የተባለ ሲሆን በአገራችን የቅኔ ባህል ዙሪያ ባለ ቅኔው ዶ/ር ታደለ ገድሌ የቅኔ ዲስኩር ያቀርባሉም ተብሏል፡፡
በዕለቱ የኪነ ጥበብ አፍቃሪ በነፃ ምሽቱን እንዲታደም ግብዣ ቀርቧል፡፡

     70 ሺህ ሄክታር እርሻ እና ከ100 በላይ የአልማዝና ወርቅ ማምረቻ ፈቃድ አላቸው

      የኮንጎው ፕሬዚዳንት ጆሴፍ ካቢላ እና ቤተሰባቸው በአገር ውስጥና በውጭ አገራት በሚንቀሳቀሱ መሪ ከ80 በላይ ታላላቅ የንግድ ኩባንያዎች ውስጥ ጠቀም ያለ የባለቤትነት ድርሻ እንዳላቸውና አጠቃላይ ሃብታቸው በአስር ሚሊዮኖች ዶላር እንደሚቆጠር ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ተቀማጭነቱ በአሜሪካ የሆነው ኮንጎ ሪሰርች ግሩፕ የተባለው የጥናት ተቋም ያወጣውን የጥናት ውጤት ጠቅሶ ሮይተርስ ከትናንት በስቲያ ባወጣው ዘገባ እንዳለው፣ ጆሴፍ ካቢላ እና ቤተሰባቸው በኩባንያዎቹ ውስጥ ካላቸው የባለቤትነት ድርሻ በተጨማሪ፣ 70 ሺህ ሄክታር የእርሻ መሬትና አልማዝና ወርቅ ማምረት የሚያስችሉ ከ100 በላይ የማዕድን ፍለጋ ንግድ ፈቃዶች አሏቸው፡፡
በ2001 አባታቸውን ተክተው ወደ ስልጣን መምጣታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ምንም እንኳን የስልጣን ዘመናቸው ያበቃው ባለፈው ታህሳስ ወር ላይ ቢሆንም፣ ስልጣኔን አልለቅም ብለው በመሪነታቸው መቀጠላቸውን አመልክቷል፡፡
በተያያዘ ዜናም በሙስና ከፍተኛ የህዝብ ገንዘብ መዝብረዋል በሚል ክስ የተመሰረተባቸውን የናይጀሪያ የቀድሞ የነዳጅ ሚኒስትር ዲዛኒ አሊሰን ማዱኬ ጉዳይ ሲመረምር የቆየው ፍርድ ቤት፣ የግለሰቧን 37 ሚሊዮን ዶላር የሚገመት ንብረት እንዳይንቀሳቀስ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡
ፍርድ ቤቱ ውሳኔውን ያስተላለፈበት እጅግ ዘመናዊ ቤት ሲሆን፣ ለንደን ውስጥ በቁጥጥር ስር ከዋሉ በኋላ በዋስ ተፈትተው በዚያው የሚገኙት የቀድሞዋ ሚኒስትር ቤቱን የገዙት ከመንግስት ካዘና ያለአግባብ በመዘበሩት 37.5 ዶላር ነው መባሉን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡

  ከዘመናችን የአለም ታላላቅ የሂሳብ ሊቃውንት አንዷ እንደሆነች የሚነገርላት እና የሂሳብ የኖቤል ሽልማት ተብሎ የሚታወቀውን የፊልድስ ሜዳል ሽልማት በማግኘት የመጀመሪያዋና ብቸኛዋ የአለማችን ሴት የሆነቺው ኢራናዊቷ መሪየም ሚርዛካኒ በጡት ካንሰር ህመም በ40 አመቷ ማረፏ ተዘግቧል፡፡ ላለፉት ለአራት አመታት ያህል በጡት ካንሰር ስትሰቃይና ህክምናዋን ስትከታተል የቆየቺው ኢራናዊቷ የስታንፎርድ የሂሳብ ፕሮፌሰር መሪየም ሚርዛካኒ ባለፈው ቅዳሜ ለህልፈተ ህይወት መዳረጓን ሜይል ኤንድ ግሎብ ዘግቧል፡፡ መሪየም ሚርዛካኒ ኮምፕሌክስ ጂኦሜትሪ እና ዳይናሚክ ሲስተምስ በተባሉ ዘርፎች ባፈለቀቻቸው እጅግ ገራሚ ግኝቶቿ የሂሳብ የኖቤል ሽልማት ተብሎ የሚታወቀውንና በመስኩ የላቀ አስተወጽኦ ላበረከቱ ላላላቅ ተመራማሪዎችና መምህራን የሚሰጠውን የፊልድስ ሜዳል ሽልማት እ.ኤ.አ በ2014 ማግኘቷን ያስታወሰው ዘገባው፣ እስከ ዕለተ ሞቷ ድረስ በስታንፎርድ ዩኒቨርሲቲ የሂሳብ መምህርት ሆና ስታገለግል መቆየቷንም አመልክቷል፡፡
በቴህራን በሚገኘው ሻሪፍ ዩኒቨርሲቲ እና በሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ ትምህርቷን የተከታተለቺው መሪየም፣ የኢራን አለማቀፍ የሂሳብ ኦሎምፒያድ ሽልማት አሸናፊ ከመሆኗ በተጨማሪ የተለያዩ በርካታ አለማቀፍ ሽልማቶችን ማግኘቷንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ባለፈው የፈረንጆች አመት 2016 በአለማችን የተለያዩ አገራት የሚገኙ 12.9 ሚሊዮን ህጻናት ምንም አይነት የክትባት አገልግሎት አለማግኘታቸውንና ይህም ክትባት ያላገኙ ህጻናትን ለከፉ በሽታዎች ያጋልጣል ተብሎ እንደሚሰጋ የአለም የጤና ድርጅት አስታውቋል፡፡
ድርጅቱ ሰሞኑን ባወጣውና የ194 የአለማችን አገራትን የክትባት ሽፋን ደረጃ በሚያሳየው ሪፖርት እንዳለው በአመቱ ከአለማችን 10 ህጻናት አንዱ ምንም አይነት ክትባት ያላገኘ ሲሆን፣ በ8 የአለማችን አገራት ከሚገኙ ህጻናት በ2016 አመት የክትባት አገልግሎት ያገኙት ከግማሽ በታች ናቸው፡፡
አነስተኛ የህጻናት ክትባት አገልግሎት ካለባቸው የአለማችን አገራት መካከል በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሱት የአፍሪካ አገራት እንደሆኑ የጠቆመው ሪፖርቱ፣ የክትባት አገልግሎት መስፋፋት ለመቻሉ ፖሊዮን የመሳሰሉ በሽታዎች በወረርሽኝ መልክ እንዲከሰቱ ሰበብ ሊሆን ይችላል ብሏል፡፡
ተጨማሪ 6.6 ሚሊዮን ያህል የአለማችን ህጻናትም ዲቲፒ የተባለውን የክትባት አይነት ለመጀመሪያ ዙር ከወሰዱ በኋላ፣ ቀሪ ሁለት ዙር ክትባቶችን ሳያገኙ መቅረታቸውን ሪፖርቱ ጠቁሟል፡፡
ክትባት በአለማችን ተቅማጥንና ቲታነስን ጨምሮ በተለያዩ የበሽታ አይነቶች ሳቢያ በየአመቱ ሊከሰቱ ይችሉ የነበሩ 3 ሚሊዮን ያህል የህጻናት ሞቶች እንዳይከሰቱ እያደረገ ይገኛል ያለው ሪፖርቱ፣ ባለፉት 10 አመታት በአገራት መካከል ያለው የክትባት ሽፋን ልዩነት በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉንም አመልክቷል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ በአለማቀፍ ደረጃ የተሟላ የጤና አገልግሎት አቅርቦትን ለማሟላት የተያዘውን የዘላቂ ልማት ዕቅድ ግብ ለማሳካት፣ በየአመቱ 371 ቢሊዮን ዶላር ያህል ገንዘብ መመደብ እንደሚያስፈልግ የአለም የጤና ድርጅት አስታውቋል፡፡
መንግስታት፣ ለጋሾችና በጎ አድራጊዎች በየአመቱ የተጠቀሰውን ያህል ገንዘብ መድበው ከሰሩ እስከ 2030 ድረስ 97 ሚሊዮን ያህል ሰዎችን በበሽታ ለህልፈተ ህይወት ከመዳረግ ሊያድኑ እንደሚችሉ የጠቆመው ድርጅቱ፣ ለአብዛኞቹ አገራት ይህን ያህል ገንዘብ መመደብ አዳጋች በመሆኑ ለጋሾች ድጋፋቸውን መስጠት እንደሚኖርባቸውም አመልክቷል፡፡

    • የበቆጂ አትሌቶች ለኢትዮጵያ ባለፉት 20 ዓመታት 10 የኦሎምፒክ የወርቅ ሜዳልያዎች ተጎናፅፈዋል፡፡ 15 የዓለም አትሌቲክስ ሪከርዶች አስመዝግበዋል፡፡ እንዲሁም ከ34 በላይ        የዓለም ሻምፒዮና የወርቅ ሜዳልያዎችን ሰብስበዋል፡፡
    • ጥሪዎች ለበቆጂ ሯጮች ትንሳዔ ከጋዜጠኛ፤ ከከንቲባ ፤ ከእውቅ አሰልጣኞች…
    • በመላው ኢትዮጵያ ትልልቅ የስፖርት መሰረተ ልማቶች ተገንብተዋል፡፡ በቆጂ ግን የረባ ስታድዬምና የመሮጫ ትራክ የላትም፡፡ ለምን ?
    • አትሌቲክስ ኢንቨስትመንት ነበር… ግን የታላላቅ አትሌቶች መቆጠብ፤ የበቆጂ የተሰጥኦ አካባቢነት መዘንጋት

     ባለፉት 25 ዓመታት በታላላቅ የዓለማችን የአትሌቲክስ ውድድሮች ላይ ለኢትዮጵያ የላቁ ውጤቶችን እያስመዘገቡ ቆይተዋል፡፡  ትውልዳቸው በአርሲ  አሰላ፣ በቆጂና ሌሎች የገጠር ከተሞች ናቸው፡፡ በረጅም ርቀት  10ሺ  እና 5ሺ ሜትር፤ በመካከለኛ ርቀት የአትሌቲክስ ውድድሮች ዓለምን ተቆጣጥረዋል፡፡ በማራቶንና በጎዳና ላይ ሩጫዎች በሚያስመዘግቧቸው ውጤቶችም የገነኑ  ናቸው፡፡
አንድ ጣሊያናዊ ጋዜጠኛ የሯጮች ከተማ በሚል በሰራው የፎቶ ቡክሌት የበቆጂ ጉብኝቱን አስመልክቶ  ‹‹…. የዓለማችንንን ምርጥ ማራቶን ሯጮች የልደት ምስክር ወረቀቶች ቢመረመሩ በቆጂ ተደጋግማ ትጠቀሳለች…›› በሚል መፃፉን መጥቀስ ይቻላል፡፡
በ10ሺ ሜትር የአፍሪካን ፈር ቀዳጅ ድል ያስመዘገበችው ደራርቱ ቱሉ፤ በዓለም አትሌቲክስ የረጅም ርቀት ንጉስ ለመባል የበቃው ኃይሌ ገብረስላሴ፤ በ10ሺሜ፤ በ5ሺ ሜትር የማይሰበር ክብረወሰን የያዘው ቀነኒሳ በቀለ፤ በኦሎምፒክ ማራቶን ልዕልቷን ወደ አገራቸው የመለሱት ገዛሀኝ አበራና ፋጡማ ሮባ እንዲሁም ቲኪ ገላና፤ ፤ የዓለማችን የምንግዜም ምርጥ የረጅም ርቀት ሯጭ የተባለች ባለከፍተኛ ውጤት ባለቤት ጥሩነሽ እና የዘመኑ ምርጥ ፕሮፌሽናል ኢትዮጵያዊ አትሌት ገንዘቤ ዲባባ፤ ፈጣኑ የኢትዮጵያ አትሌት መሃመድ አማን  ሌሎችም ከአርሲዎቹ የገጠር ከተሞች ተገኝተዋል፡፡ በአጠቃላይ በኦሎምፒክ፣ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና፣ በዓለም አገር አቋራጭ፣ በአፍሪካ ሻምፒዮና፤ በመላው አፍሪካ ጨዋታዎች እና ሌሎች ዓለም አቀፋዊ እና አህጉራዊ ውድድሮች ከ67 በላይ የወርቅ ሜዳሊያዎችን ለኢትዮጵያ ሰብስበዋል፡፡  
ከአዲስ አበባ በ230 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኘው በቆጂ በተለይ የምትነሳ ናት፡፡ ደራርቱ ቱሉ በጣዕሜ ፤ ፋጡማ ሮባ በመራሮ፣  ጥሩነሽ ዲባባ በጨፋ፣ ቀነኒሳ በቀለና፣ ታሪኩ በቀለ፣ ቲኪ ገላናና፣ እልፍነሽ ዓለሙ በሌሙ፣ የተወለዱባቸው የገጠር መንደሮች ናቸው፡፡ የበቆጂን ዙርያዋና ከበዋታል።  የበቆጂ አትሌቶች ለኢትዮጵያ ባለፉት 20 ዓመታት 10 የኦሎምፒክ የወርቅ ሜዳልያዎች ተጎናፅፈዋል፡፡  15 የዓለም አትሌቲክስ ሪከርዶች አስመዝግበዋል፡፡ እንዲሁም ከ34 በላይ የዓለም ሻምፒዮና የወርቅ ሜዳልያዎችን ሰብስበዋል፡፡
 በአንድ ወቅት አንድ ታዋቂ የቱርክ ጋዜጠኛ እንደጻፈው በቆጂ እንደ  አገር በመቆጠር በዓለም የአትሌቲክስ መድረክ ምን ያህል የገዘፈች መሆኗን በንፅፅር መመልከት ይቻላል፡፡  ባለፉት 25 ዓመታት በኦሎምፒክ መድረክ ከ60ሺ ነዋሪዎች ከሚገኙባት በቆጂ የወጡ አትሌቶች የሰበሰቧቸው ሜዳልያዎች  1.2 ቢሊዮን ህዝብ ያላት ህንድ በሁሉም ስፖርቶች በኦሎምፒክ ከሰበሰበቻቸው ሜዳልያዎች የሚበልጥ፤ 247 ሚሊዮን ህዝብ ካላት ኢንዶኔዥያ በእጥፍ የሚልቅ ነው፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፡፡ ለናሙና ያህል ብቻ የዲባባ እህትማማቾች በኦሎምፒክ መድረክ ያገኟቸው የወርቅ ሜዳልያዎች ብዛት 22 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ሶሪያ እና 28 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ሳውዲ አረቢያ በድምር ከሰበሰቡት የሚበልጥም ነው፡፡ በኢትዮጵያ አትሌቲክስ በዓለም ሻምፒዮና፤ በኦሎምፒክ እና በዓለም አገር አቋራጭ ትልቁን ውጤት ያስመዘገበችው ጥሩነሽ ዲባባ የሰበሰበችው የወርቅ ሜዳልያ ብዛት 179 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ፓኪስታን እንኳን አላስመዘገበችውም፡፡
በዚህ ከፍተኛ ስኬት የኢትዮጵያ ክብር በዓለም አትሌቲክስ በወርቃማ ቀለም እንዲሰፍር ሆኗል፡፡ በቆጂን በዓለም አቀፍ ደረጃ የምትታወቅ የሯጮች ምድርም  አድርጓታል።
የአትሌቶቹ ውጤታማነት ላይ በየጊዜው በአትሌቲክስ ባለሙያዎች ምርምሮች እየተደረጉባት ይገኛል፡፡  በመላው ዓለም በሚሰራጩ ትልልቅ ሚዲያዎች  በተደጋጋሚ የምትጠቀስ ከተማ መሆኗም ቀጥሏል፡፡ በየጊዜው ልዩ ዘጋቢ ፊልሞች ተሰርተውላታል፡፡  በተለያዩ ጊዜያት ስለሚወጡባት ታላላቅ አትሌቶቿ፤ ስለመልክዓምድሯ፤ ስለአየር ንብረቷ፤ ስለ አትሌቶች አኗናር፤ ስልጠና እና የእለት ተዕለት ህይወት በስፋት እየተወሳ ነው፡፡  
ጥሪ ከጋዜጠኛው
በ1ኛው «አረንጓዴ ልማት ለአረንጓዴ ጎርፍ» የጎዳና ሩጫ መነሻነት… በቆጂን በአትሌቲክስ ለማልማት
የታላላቅ  አትሌቶች መገኛ በሆነችው በቆጂ ከተማ  ለመጀመሪያ ጊዜ  የ5ነ ኪሜ የጎዳና ላይ ሩጫ «አረንጓዴ ልማት ለአረንጓዴ ጎርፍ» በሚል መርህ ከወር በፊት ተዘጋጅቶ ነበር። ከበቆጂ 80ኛ ዓመት ክብረ በዓል ጋር ተያይዞ  በተካሄደው ውድድር ከአምስት ሺ በላይ የከተማዋ ነዋሪዎች እንዲሁም አትሌቶች ተሳትፈዋል፡፡ የከተማዋ የሩጫ ባህል ሆኖ የ5ኪ ሜትር ውድድሩ በአትሌቶች መካከል ከፍተኛ ፉክክር የተደረገበት ሲሆን ተሳታፊው ህዝብም  ችግኝ ይዞ በመሮጥ ድምቀት ሰጥቶታል፡፡
የጎዳና ላይ ሩጫው ጭላሎ ሚዲያ ፕሮሞሽን በተባለ ድርጅት የተዘጋጀ ነው፡፣፡ ጭላሎ በበቆጂ ገዝፎ የሚታይ ልዩ ግርማ ሞገስ ያለው ተራራ ነው፡፡ የድርጅቱ ባለቤት   ጋዜጠኛ እና ገጣሚ አንዱዓለም ጌታቸው ነው፡፡ ተወልዶ ያደገው በቆጂ ላይ ነው፡፡ ስለበቆጂ ልጆች አስተዳደግ እና የሩጫ ባህል ለስፖርት አድማስ ሲገልፅ‹‹ እንደማንኛውም የከተማዋ ተወላጅ ልጅነቴን ያሳለፍኩት በእረኝነት ነው ፡፡ ቤተሰብ  ሲልክህ ሮጥ ብለህ  ይባላል፡፡ ወደ ተላክበት የምትሮጠው ብዙ ርቀት ነው። ሽርካ የተባለች የገጠር ከተማ ወደ የሚኖሩ አያቶቼ ቤት ስላክ አስታውሳለሁ፡፡ 3 ሰዓታት ይወስድብኛል፡፡ አብዛኛውን እየሮጥኩ ነበር የምሸፍነው፡፡ ስለዚህ ሩጫ የልጅነት ህይወታችን አካል ነው፡፡ የከተማዋ ባህል ሆኖ አድገንበታል፡፡ …የሁሉ መነሻ  ከ25 ዓመታት በፊት የደራርቱ ቱሉ በባርሴሎና ኦሎምፒክ ለኢትዮጵያ እና ለአፍሪካ ፈርቀዳጅ ድል ማስመዝገቧ ነበር። ያኔ በቆጂ የነበረ ትውልድ በሙሉ ሯጭ መሆንን ተመኘ፡፡›› ብሏል።
አንዱዓለም እነ ቀነኒሳ፤ የዲባባ እህትማቾችና ሌሎችም ምርጥ አትሌቶች በተማሩበት ትምህርት ቤት ስለነበረው የሩጫ ትጋት እና ፍቅር ትውስታ አለው፡፡ በተለይ በእረፍት ሰዓት በተማሪዎች መካከል ይደረጉ የነበሩ ውድድሮች ናቸው። በቆጂ ዛሬም ድረስ ሩጫን  ባህሏ ያደረገች  ልዩ ከተማ ናት። በትምህርት ቤቶች ብቻ አይደለም፡፡ በከተማዋ ዙርያ ገብ በሚገኙ ጫካዎች፤ የተንጣለሉ መስኮች እና ጋራዎች ልምምድ እና ስልጠና የተለመዱ ትእይንቶች ናቸው፡፡
ጋዜጠኛ አንዷለም ምንም እንኳን ገና በታዳጊነቱ የሩጫ ህልም ቢኖረውም ብዙ አልገፋበትም፡፡ በከተማዋ ሚኒ ሚዲያዎች ግን ስለ በቆጂ ታላላቅ አትሌቶች ገድል በመዘገብ ወደ ጋዜጠኝነት ሙያ አድልቶ ነበር፡፡ በከተማዋ ከአትሌቲክስ ጋር የተያያዙ ስራዎችን ለማከናወን ሲተጋ  ቆይቷል፡፡ ‹‹ በቆጂ የስሟን ያህል ትኩረት አላገኘችም፡፡ በስፖርት መሰረተ ልማቶች እጅግ ኋላ ቀር ናት፡፡ ስለዚህም ይቆጨኛል፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ ስሟ በገነነ የሯጮች ምድር  ሁለገብ ስታድዬም፤ የማሰልጠኛ ማዕከልና የመሮጫ ትራክ አለመኖሩ ተገቢ አይደለም፡፡ የዛሬ አስር ዓመት  የኢትዮጵያ አትሌቶች ሙዚዬም በከተማዋ ሊገነባ መሰረት ተጥሎ ተግባራዊ አልሆነም፡፡ይህን ለመቀየር ነው የበኩሌን ጥረት ማድረግ የጀመርኩት፡፡›› በማለት የተነሳበትን ዓላማ ለስፖርት አድማስ አስረድቷል፡፡
ስለዚህም አንዷለም ጌታቸው ለከተማዋ ባደረበት ቁጭት የጎዳና ላይ ሩጫውን ለማዘጋጀት እንዲወስን አድርጎታል፡፡ ጭላሎ ሚዲያ የተባለ ድርጅቱን ካቋቋመ በኋላ በመጀመርያ ለ2009 የገና በዓል የአትሌቶች መንደር በሚል ልዩ የቴሌቭዥን ፕሮግራም አዘጋጀ፡፡ በቆጂ ማናት የሚለውን ጥያቄ መልስ ለመስጠት በተዘጋጀው በዚህ ልዩ ስነስርዓት እንደመዝናኛ የሙዚቃ ከንሰርት ከማዘጋጀቱም በላይ እነ ኃይሌ፤ ገዛሐኝ አበራ እና ሌሎች ትልልቅ አትሌቶች በክብር እንግድነት የተሳተፉበት ነበር፡፡ ከዚህ ተመክሮው በኋላ እንዷለም የመጀመርያውን የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር በከተማዋ ሊያስተናግድ ችሏል። የአትሌቶች መገኛ የሆነች ታሪካዊ ከተማ እንዴት ስፖርተኛ ህዝቧን የሚያሳትፍ ውድድር አይኖራትም በሚል ቁጭት በቀረፀው ፕሮጀክት ነው፡፡«አረንጓዴ ልማት ለአረንጓዴ ጎርፍ» በሚል መርህ በስኬት የተካሄደውን የጎዳና ላይ ሩጫ በየዓመቱ ለመቀጠል እንደሚፈልግ ያሳወቀው አንዷለም፤ በተለይ በአየር ንብረት ለውጥ የዓለማችን ታላላቅ አትሌቶች የተገኙባት በቆጂ ከተማ ተጎጂ መሆኗን ለዓለም ለማሳወቅ የሚያስችል ፈርቀዳጅ ሃሳብ በመሆኑ ውጤታማነቱን ያመለክታል ብሏል፡፡
አትሌቲክስ ስታድዬም በሚል ስያሜ ያልተሟላ መሰረተ ልማት እንደሆነ ቀጥሏል፡፡ ትራክ የሌለው አጥር የለሌለው የበቆጂ ስታድዬም፡፡ በሌላ በኩል የበቆጂ አትሌቲክስ ማሰልጠኛ ማዕከልም በተሟላ ግንባታና መሰረተ ልማት የሚንቀሳቀስ አይደለም፡፡ በአጠቃላይ እነዚህ የስፖርት መሰረተ ልማቶች በትኩረት ተገንብተው የሚንቀሳቀሱ አለመሆናቸው ከባድ ቁጭት የሚፈጥርብኝ ነው፡፡ እውነቱን ለመናገር የኢትዮጵያ አትሌቲክስ የውጤት መውረድ እና የላቀ ብቃት ያላቸው አትሌቶች በተተኪነት የማፍራት እድል የተበላሸው ከእነዚህ ሁኔታዎች ጋር ተያይዞ ይመስለኛል፡፡›› በማለት አንዷለም ጌታቸው ለበቆጂ ከተማ የሚሰማውን ቁጭት ይገልፀዋል። በርግጥ የበቆጂ አትሌቶች ከስታድዬሙ እና ከማሰልጠኛ ማዕከሉ ይልቅ በተፈጥሯዊ መልክዓ ምድሮችን መስራት ይመርጣሉ ግን የስፖርት መነሰረተ ልማቶች መገንባት አለባቸው፡፡

ጥሪ ከከንቲባው
ለኢትዮጵያ ሆነ ለአፍሪካ ከፍተኛ ውጤት የሚያስመዘግቡ  አትሌቶችን ለማፍራት
 የበቆጂ ከንቲባ አቶ ሽመልስ ተስፋዬ ለጋዜጠኞች በሰጡት አስተያየት  1ኛው «አረንጓዴ ልማት ለአረንጓዴ ጎርፍ» የጎዳና ላይ ሩጫው የበቆጂን 80 ዓመት ከመዘከሩም በላይ ከውድድሩ ጎን ትልልቅ አጀንዳዎች በማንገብ በመከናወኑ አስደስቶናል ይላሉ፡፡ የአየር ንብረት ለውጥን ለመዋጋት የሚደረግ ዘመቻን ለማፋፋም፤ በአትሌቲክስ እየተንሰራፋ የመጣውን የዶፒንግ ችግር ተመለከተ የግንዛቤ እና የማስተማርያ መድረክ ለመፍጠር እንዲሁም ዜግነታቸውን የሚቀይሩ አትሌቶች እየበዙ መምጣታቸውን ተቃውሞ ለውጥ ለመፍጠር የሚደረጉ  ጥረቶችን ያስተዋወቅንበት መድረክ ስለሆነ በማለትም ማስረጃቸውን አቅርበዋል፡፡
‹‹በቆጂ የማትነጥፍ የአትሌቲክስ ስኬት ምንጭ ሆና እንድትቀጥልና ተከታዮችን ለማፍራት ታላላቅ አትሌቶች ያላቸው ምሳሌነት አስተዋፅኦ ቢኖረውም ገና ብዙ መስራት ይጠበቅብናል፡፡›› የሚሉት ከንቲባው ‹‹አትሌቶች የሚጠበቅባቸውን ያህል ሰርተዋል ብሎ የከተማው መስተዳድርም ሆነ ህዝቡ አያምንም፡፡ ከተማዋ ጥሩ ስታድዬም፤ የልምምድ ማዕከል እንኳን የላትም፤ ይህ ደግሞ መቀየር አለበት ሲሉ ይናገራሉ፡፡ በከተማው መስተዳድር፤ በወጣቶችና ስፖርት፤ በአትሌቲክስ ፌደሬሽንነና በሌሎች ባለድርሻ አካላት የተከናወኑ ጅምር ተግባራት መኖራቸውን አያይዘው የጠቀሱት ከንቲባው በቆጂ ላይ ደረጃውን የጠበቀ ስታድዬም እንዲሁም የልምምድ እና ማሰልጠኛ ማዕከል መገንባት ለኢትዮጵያ ሆነ ለአፍሪካ ከፍተኛ ውጤት ሊያስመዘግቡ የሚችሉ አትሌቶችን ለማፍራት የሚያስችል ነው ይላሉ፡፡
‹‹ታላላቆቹ አትሌቶች በስፖርቱ ካገኙት ክብር እና አንፃር እንዲሁም በኢኮኖሚ ካላቸው አቅም ጋር ተያይዞ በቆጂ ላይ ብዙ ሊሰሩ ይችላሉ፡፡ ይህን አስመልክቶ በየጊዜው ውይይት እያደረግን ቆይተናል፡፡ የአትሌቶችን ተግባራዊ ምላሽ እየተጠባበቅን ነው፡፡ ከዚህ በፊት በከተማው አስተዳደር በኩል ለአትሌቶቹ የተለያዩ ማበረታቻዎችን በማድረግ ሰርተናል፡፡ በአሰላ ከተማ የንግድ ማዕከል፤ ሆቴል የሰሩ አሉ፡፡ የከተማው መስተዳድር ከዚህ በፊት ለተለያዩ የልማት ስራዎች ይሆናል በሚል መሬቶችን ለአትሌቶች ሰጥቶ ነበር፡፡ ታላላቆቹ አትሌቶች በሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች የምንሰራቸው የግንባታ ስራዎች እስኪጠናቀቁ ግዜ ስጡን ብለው ስለነበር እንጅ። አትሌቶች ለእኛ አምባሳደሮቻችን ምልክቶቻችን ናቸው። የከተማው መስተዳድር አብሯቸው ለመስራት ይፈልጋል። እነሱም ፍላጎት እንዳላቸው እናውቃለን፡፡›› ብለዋል የበቆጂ ከንቲባ አቶ ሽመልስ ተስፋዬ፡፡
የከተማው መስተዳድር በተለያዩ ክለቦች፤ በግብረሰናይ ተቋማት የተያዙ የአትሌቲክስ ፕሮጀክቶች እንደሚከታተል የከተማው ከንቲባ ተናግረው፤  የኦሮምያ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ የሚያንቀሳቅሰው የበቆጂ ማሰልጠኛ ማዕከልም በመንግስት በጀት ተገንብቶ ከተለያዩ ስፍራዎች ተሰጥኦ ያላቸውን አትሌቶች በመመልመል በቂ ስልጠና በመስጠት እየሰራ መሆኑን፤ የብዙ ቀደምት አትሌቶች ዛሬም ቢሆን ዋና መገኛዎች ትምህርት ቤቶች በመሆናቸው በዚያም ሰፊ ተግባር ለማከናወን እንቅስቃሴ አለ የሚሉት ከንቲባው በአጠቃላይ ግን በተሟላ ጥራት እና ብቃት እየሰራን ስላልሆንን ይህን በከፍተኛ ንቅናቄ ለመቀየር ትኩረት አድርገናል ብለዋል፡፡
ይቀጥላል

-------------------------------------------------
                          
                         የአፍሪካ ዋንጫን በቻይና ወይም በአሜሪካ የማዘጋጀት ሃሳብ ቀርቧል

      የ2023 የአፍሪካ እግር ኳስ ዋንጫ ውድድርን በቻይና፣ በአሜሪካ ወይም በኳታር ለማዘጋጀት እና ከአህጉሪቱ ውጭ የሚገኙ 3 አገራት ብሄራዊ ቡድኖችን በውድድሩ ለማሳተፍ የሚያስችል ምክረ ሃሳብ በአፍሪካ የእግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን ካፍ ስብሰባ ላይ መቅረቡ ተዘግቧል፡፡
ካፍ የአፍሪካ የአግር ኳስ ዋንጫን የገንዘብ አቅም ለማጠናከርና ውድድሩን የበለጠ ሳቢነት ያለው ለማድረግ በሚቻልበት ሁኔታ ዙሪያ ለመምከር ባለፈው ማክሰኞ እና ረቡዕ በሞሮኮ ባካሄደው ስብሰባ ላይ የቀረበው ይህ ምክረ ሃሳብ፣ የ2023ን የአፍሪካ ዋንጫ እንዲያዘጋጁ ቻይናን፣ አሜሪካን ወይም ኳታርን የመጋበዝ አማራጭን ያቀረበ ነው፡፡ የገንዘብ አቅምን ማጠናከርንና የአፍሪካ ዋንጫን አለማቀፋዊ ማድረግን ግቡ ያደረገ ነው የተባለው ምክረ ሃሳቡ፣ በመገናኛ ብዙሃን በስፋት መሰራጨቱን ተከትሎ በበርካታ የማህበራዊ ድረገጽ ተጠቃሚዎች ትችት እየተሰነዘረበት ይገኛል፡፡
ሃሳቡ በካፍ ተቀባይነት የማግኘቱ ዕድል ጠባብ መሆኑን የዘገበው ጋና ሶከር ኔት ድረገጽ፣ የ2023 የአፍሪካ ዋንጫን የማስተናገድ ተራውን ለጊኒ ቀደም ብሎ መስጠቱንም አስታውሷል፡፡

  • የኢትዮጵያና እስራኤል ግንኙነት እስከ 3 ሺህ ዓመት ይዘልቃል
                                        • ለሁሉም ቤተ-እስራኤላውያን እስራኤል አገራቸው፤ ቤታቸው ናት
        ተወልደው ያደጉት በደቡብ ጎንደር አምቦ በር በተባለች የገጠር ቀበሌ ውስጥ ነው፡፡ በህጻንነታቸው እንደ ማንኛውም ገጠር ተወልዶ እንዳደገ ልጅ፤ ቤተሰቦቻቸውን እንጨት በመልቀም፣ ውሃ ከምንጭ በመቅዳትና በመላላክ እንዳገለገሉ ይናገራሉ፡፡ መብራት እንኳን በሌለበት የገጠር ቀበሌ ያደጉት የዛሬዋ እንግዳችን፤ በ16 ዓመት ዕድሜያቸው ወደ እስራኤል በማቅናት ከአገራቸውና ቀዬአቸው ርቀው፣ በሂብሩ ቋንቋ ትምህርት በመጀመራቸው የገጠማቸውን ፈተና
አጫውተውናል፡፡ በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደር የሆኑት ክብርት አምባሳደር በላይነሽ ዘባዲያ፤ የዛሬ ሳምንት ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ሲያስመርቅ፣ በክብር እንግድነት ተገኝተው ነበር፡፡ ለተመራቂዎችም የማነቃቂያ ንግግር አድርገዋል፡፡ በስፍራው የተገኘችው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ በአምባሳደሯ
ትውልድና እድገት፣ በእስራኤል ቆይታቸው ስለተጋፈጧቸው ፈተናዎች፣ ለአምባሳደርነት እስከመድረስ ስላበቋቸው የጥንካሬ ምስጢሮች፣ ስለ ኢትዮጵያና እስራኤል ግንኙነት፣ በቤተ- እስራኤሎች የኑሮ ዘይቤና የመብት ጥሰቶች ዙሪያ (እጅግ በተጣበበ ሠዓታቸው) አምባሳደር በላይነሽ ዘባዲያን አነጋግራቸዋለች፡፡ እነሆ፡-

      ተወልደው ባደጉበት አካባቢ ዩኒቨርስቲ ተከፍቶ፣ እርስዎም የክብር እንግዳ ሆነው፣ ተማሪዎችን ሲያስመርቁ ምን ተሰማዎት?
እምም. . . በጣም ነው ደስ ያለኝ፡፡ እንዲያውም ልንገርሽ… ከተመራቂዎቹ በላይ እኔን ደስ ብሎኛል። ምክንያቱም እኔ እዚህ በማድግበት ጊዜ ዩኒቨርስቲ ቀርቶ ብዙ የትምህርት ዕድል አልነበረም፡፡ ደስታዬን እጥፍ ያደረገው አንቺ እንዳልሽው እዚህ አካባቢ ተወልጄ አድጌ፣ በዚህ ሀገር ወግና ባህል ታንፄ፣ ከዚያም ወደ እስራኤል አገር ሔድኩኝ፡፡ በወቅቱ ት/ቤት ስገባ የመማሪያ ቋንቋው እንኳን እንግሊዝኛ አልነበረም፤ ሂብሩ ነበር፡፡ አንዳንዴ መምህራን ሲያስተምሩ  አይገባኝም ነበር፡፡ መጀመሪያ በአማርኛ ጽፌ፣ ከዚያ ወደ መኝታዬ እሔድና ያንን ጽሑፍ ወደ እንግሊዝኛ እቀይራለሁ፡፡ ከዚያ ነው በስንት ልፋት ወደ ሂብሩ የምቀይረው፡፡ እኔ በእንደዚያ ዓይነት አስቸጋሪና ፈታኝ ጊዜ ነበር ያለፍኩት፡፡ ያንን ችግር የተጋፈጥኩት መማር ስለነበረብኝ ነው፡፡  
ተምረው ትልቅ ደረጃ ለመድረስ የነበረውን ህልም ከየት ነው የታጠቁት?
እኛ ቤተሰቦቻችን ያሳደጉን “ጠንክራችሁ ከተማራችሁ ትልቅ ደረጃ ትደርሳላችሁ፤ ለአገራችሁም ኩራት ትሆናላችሁ” በሚል ምክር ነበር፡፡ ይህንን ተከትዬ አስቸጋሪ ፈተናዎችን አልፌ እዚህ ደርሻለሁ፡፡ ስለዚህ ይህንን ስንቅ ያስታጠቁኝ ቤተሰቦቼ ናቸው፡፡ ሌላውም ወጣት ምንም ፈተና ቢገጥመው፣ ዓላማ ካለው የፈለገበት መድረስ ይችላል፡፡ እርግጠኛ ነኝ ዛሬ በደብረታቦር ዩኒቨርስቲ ይህቺን አገር የሚለውጡ ብዙ ራዕይ ያላቸው ተማሪዎች በአካባቢያቸው፤ በራሳቸው ቋንቋና በወገኖቻቸው ተምረው ተመርቀዋል፡፡ እኔም ተወልጄ ባደግሁበት አካባቢ፣ ያውም ዩኒቨርስቲ ተከፍቶ፣ እኔም እዚህ ደርሼ፣ በክብር እንግድነት ተጋብዤ ተማሪዎችን ስመርቅ፣ ከእነርሱ በላይ መደሰቴ ለዚህ ነው፡፡ አሁንም የምመክረው፣ ዓላማ ካላችሁ የትም ትደርሳላችሁ፤ እኔን ተመልከቱ የሚል ነው፡፡ በምረቃው ላይ ያስተላለፍኩትም መልዕክት ይሔው ነው፡፡
እንደሚያውቁት በተለይ በገጠሩ የአገራችን ክፍል፣ ሴት ልጅ ያለ ዕድሜ ጋብቻን ጨምሮ በርካታ ፈተናዎችን ትጋፈጣለች፤ ዛሬ እነዚህን ፈተናዎች አልፋ ከተመረቁት 2653 ተማሪዎች፣ አጠቃላይ ብልጫ ያመጣችውን  ወጣት የሸለሙት እርስዎ ነበሩ --
እጅግ በጣም ተደስቻለሁ፡፡ ይገርምሻል እኮ ስሟ እንደኔው በላይነሽ ነው፡፡ ይሔ የሚያሳየው የራሷን ጥረትና ትግል እንዲሁም የዓላማ ፅናት ነው። አየሽ እኔም የገጠሩን አስተዳደግ አልፌበታለሁ፤ አውቀዋለሁ፡፡ ፈተናዎችን ተጋፍጠው ለዚህ የሚበቁ ልጆችን ሳይ ልቤ ይነካል፡፡ ደስታዬ ከልክ ያልፋል፡፡ አየሽ ነገ ይህቺ ልጅ የአገር መሪ ልትሆን ትችላለች፡፡ ዛሬ ያገኘችው ክብር፣ አድናቆትና ምርቃት ለበለጠ ክብርና ኃላፊነት እየገፋፋት ይሔዳል፡፡ ለሌሎች አቻዎቿም ምሳሌ ትሆናለች፡፡ ወደ ኋላም መሔድ አትፈልግም፡፡ ይህቺ ልጅ አገሪቷ በልጆቿ ተስፋ እንዳላት አመላካች ናት፡፡ ስላገኘኋት፤ ስላየኋት በጣም ደስ ብሎኛል፡፡
እስቲ ስለ አስተዳደግዎ በጥቂቱ ያንገሩኝ ?
ከጎንደር 25 ኪሎ ሜትር ገባ ብሎ በሚገኝ መንደር ነው የተወለድኩት፡፡ በጣም ጥሩ ጥሩና ጠንካራ ቤተሰብ ውስጥ ነው ያደግሁት። ትምህርትም የጀመርኩት እዚያው ሰፈር ውስጥ በነበረ ት/ቤት ነው፡፡ የእስራኤል ጂው (ቤተ እስራኤል) ከሆነ ቤተሰብ ነው የወጣሁት፡፡ አባቴ የታወቁ ትልቅ የሃይማኖት መሪ ነበሩ፤በተለይ አርብ አርብ መጽሐፍ ቅዱስ እየተነበበ፣ እንማራለን፡፡ በእኛ ሃይማኖት አርብ አርብ መሰብሰብ አለ፡፡ እራት የሚበላው በአንድ ላይ ነው፡፡ ከዚያ ለሕይወታችን የሚጠቅመንን ነገር ከመጽሐፍ ቅዱስ እያጣቀሱ አባታችን ያስተምሩን ነበር፡፡
ከያኔው የአባትዎ ትምህርት ይበልጥ ውስጥዎ የቀረውን ሊነግሩኝ ይችላሉ?
አንዳችን ሌሎችን እንደ ራሳችን ወድደን ስለመኖር፣ ተካፍለን ስለ መብላት፣ አካባቢያችንንና ሕዝቡን ስለ መውደድ፣ በአጠቃላይ ስለ አንድነትና ስለ ፍቅር ስንማር ነው ያደግነው፡፡ መማር ብቻም ሳይሆን ቤተሰብም ይህንን በተግባር ሲያደርግ ዓይቼ ነው ያደግሁት፡፡ እንዲያውም አባቴ ‹‹የእኛ ቤት እንደ አብርሃም ቤት ነው›› ይሉ ነበር፡፡ እነዚህ ትምህርቶችና ምክሮች አሁን ላለሁበት ደረጃ ቁልፍ ሚና ተጫውተዋል፡፡ የልጅነት ጊዜዬንም ከቤተሰቤ ጋር በደስታ ነው ያሳለፍኩት፡፡ ይሔ ሁሉ አሁንም ትዝ ይለኛል፡፡
እስራኤል ምንድን ነው ያጠኑት?
በዓለም አቀፍ ግንኙነት እና በአፍሪካ ጥናቶች  ነው የመጀመሪያና ሁለተኛ ድግሪዬን የሰራሁት፤ በኋላ ፒኤችዲ ልሰራ ስል የሆኑ ሰዎች ‹‹ለምን አትሞክሪም፤ ዲፕሎማት መሆን ትችያለሽ›› የሚል ሃሳብ ሲያመጡ፣ ማስተርሴን እየሠራሁ ጥናትና ምርምር ማድረግ ጀመርኩ፡፡ ምክንያቱም፤ የሠዎቹ ሃሳብ ወደ ውስጤ ሰርፆ ነበር፡፡ ከዚያ ዲፕሎማት መሆን አለብኝ ብዬ ወሰንኩኝ፡፡ ዲፕሎማት ከሆንኩ በኋላ ግን ወደዚህ እመጣለሁ ብዬ ያሰብኩት አሁን በመጣሁበት ወቅት አልነበረም፡፡ ለምን ብዙ ልምዶችን መቅሰም እንዳለብኝ አምን ነበር፡፡ የሆነ ሆኖ ያው እንደሚታወቀው የዛሬ አምስት ዓመት አምባሳደር ሆኜ መጣሁ፤ ይሄው እየሠራሁ ነው፡፡
በአንድ ወቅት የሁለቱ አገሮች ግንኙነት ተቋርጦ እንደነበርና መልሶ መቀጠሉን ሠምቻለሁ፡፡ የሁለቱ አገሮች ግንኙነት በአሁኑ ወቅት ምን ይመስላል?
ኢትዮጵያና እስራኤል በአሁኑ ወቅት ያላቸው ግንኙነት እጅግ በጣም በጣም የጠበቀ ነው። ግንኙነታቸው እስከ 3 ሺህ ዓመት ይዘልቃል፡፡ ከንጉሥ ሰሎሞንና ከንግሥት ሣባ ጊዜ ጀምሮ ማለት ነው፡፡ ሆኖም እ.ኤ.አ በ1973 ዓ.ም ጦርነት ስለነበረ ኢትዮጵያ ከእስራኤል ጋር የነበራትን ግንኙነት አቋረጠች፡፡ ግንኙነቱ እንደገና እ.ኤ.አ በ1989 ታደሰ። ግንኙነቱ ከታደሠ በኋላ ቀስ በቀስ እየተሻሻለ መጥቶ፣ አሁን ትልቅ ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡
የሁለቱ አገራት ግንኙነት ትልቅ ደረጃ ላይ መድረሱን የሚያመለክቱ ነገሮችን ሊጠቅሱልኝ ይችላሉ?
የአገራቱ ግንኙነት ትልቅ ደረጃ ላይ ስለመድረሱ ከሚያመላክቱት አንዱ፣ የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ለመጀመሪያ ጊዜ ኢትዮጵያን መጎብኘታቸው ሲሆን ባለፈው ወርም የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር እስራኤልን መጎብኘታቸው የአገራቱን የጠበቀ ግንኙነት ያመለክታል፡፡ ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽም፤ የሁለቱ አገራት ግንኙነት ከ3ሺህ ዓመታት በላይ የዘለቀ ነው፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የሁለቱ አገራት ሕዝብ የተሳሰረ በመሆኑ፣ ይህን ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር ሕዝብ ለሕዝብ፣ ዩኒቨርስቲ ለዩኒቨርስቲ፣ ሆስፒታል ለሆስፒታል ትስስር መፍጠር አለብን፡፡ እስራኤል ስፋቷና የሕዝቧ ቁጥር ትንሽ ቢሆንም ትልቅ አገር ናት፡፡ በጠላት የተከበበች ብትሆንም በዕውቀት፣ በሥራና አገር በመውደድ የጠነከሩ ሕዝቦች ስላሏት አሁንም ትልቅና ተፅዕኖ ፈጣሪ አገር ናት፡፡
ከዘመቻ ሠለሞን ጀምሮ ኢትዮጵያ ውስጥ የነበሩ በርካታ ቤተ እስራኤላውያን ወደ እስራኤል መሔዳቸው ይታወቃል፡፡ ነገር ግን ከአኗኗር፣ ከሠብዓዊ መብት አያያዝ አኳያ የሚሰሙ ቅሬታዎች አሉ፡፡ እስቲ በዚህ ላይ ማብራሪያ ይስጡኝ?
የኢትዮጵያውያን ይሁዳዎች (ቤተ እስራኤላዊያን) በእስራኤል የሚኖሩት በጣም በጥሩ ሁኔታ ነው፡፡ አንዳንድ ችግር ያለባቸውም አሉ፡፡ ስለ ጉዳዩ ሚድያው የሚያሳየውን ካጤንሽው ብዙ ጥሩ ነገር አያሳይም፡፡ አንድ ነገር ሲነሳ ነው ሔደው ያንን ብቻ ለመናገር የሚፈልጉት፡፡ እኛ አንደኛ የጀርባ ታሪካችንን (background) ማየት አለብን። አብዛኞቹ ቤተሰቦቻችን አርሰው፣ ቤተሰባቸውን የሚያስተዳድሩ፣ እጅግ የምንኮራባቸው ገበሬዎች ናቸው፡፡ እዚያ አገር ስትሔጂ ቴክኖሎጂው፤ የባህሉ ጫና አለ፡፡ ያንን ሁሉ አልፈን፣ በዚህ አጭር ጊዜ ትልልቅ ቦታ የደረሱ ልጆችን ማየት መቻላችን፣ለእኛ ትልቅ ስኬት ነው ብዬ ነው የማስበው፡፡ እርግጥ ቀደም ሲል ከጠቀስኳቸው ነገሮች፤ ጫናዎች አንፃር አንዳንድ የሚነሱ ችግሮች አሉ፡፡ እነርሱን የማለፍ ብልሀት አስፈላጊ ነው፡፡ ከዚያ በተረፈ ሁሉም ቤተ-እስራኤላዊያን፣ እስራኤል አገራቸው፤ ቤታቸው ናት። ሁሉም መብት አላቸው፡፡ እንደውም ለኢትዮጵያ ቤተእስራኤላዊያን መንግሥት ከፍተኛ ድጋፍ እያደረገላቸው ነው፡፡ ለምሳሌ ለዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ማስትሬት ወይም ዶክትሬት ዲግሪያቸውን እስኪሰሩ  ድጋፍ አይለያቸውም። ቤት መግዛት ቢፈልጉ 80 በመቶውን ወጪ የሚሸፍነው የእስራኤል መንግሥት ነው፡፡ ምክንያቱም ኢትዮጵያውያን ቤተ-እስራኤሎች ድጋፍ ያስፈልጋቸዋል፡፡ ከራሺያ የመጣው ቤተ-እስራኤላዊ ተምሮ፣ ቴክኖሎጂውን አውቆ ነው፡፡ እዚህ ኢትዮጵያ የኖርነው ደግሞ የኖርንበት ሥርዓት ሌላ ነው፡፡ ስለዚህ መደገፍ አለብን፡፡ ያንን ለማስተካከል የእስራኤል መንግሥት እየሠራ ሲሆን  ሌሎች በዚሁ ላይ የሚሰሩ ድርጅቶችም አሉ፡፡ ነገሮች በሒደት መቶ በመቶ ጥሩ ይሆናሉ፡፡


አለቃ ገብረ ሃና ከዕለታት አንድ ቀን መንገድ እሄዳለሁ ብለው ይነሳሉ፡፡
“ማዘንጊያ” ይላሉ ሚስታቸውን
“አቤት” ይላሉ ሚስት
“መንገድ ልሄድ አስቤያለሁ”
“ወዴት?”
“ወደ ቆላ ወርጄ የታመመ ጠይቄ፣ የተጣላ አስታርቄ እመለሳለሁ!”
“እንግዲያው ባዶ ሆድዎን አይሄዱም፤ ቆይ ቁርስ ደርሷል፡፡”
“ባዶ ሆዳችንን አደል የተፈጠርን?”
“ቢሆንም ወንድ ልጅ የሚገጥመው ስለማይታወቅ ባዶ ሆዱን አይወጣም”
“ሴትስ የሚገጥማት ታጣለች ብለሽ ነው? ካልሽ እንግዲህ ቶሎ አቅርቢልኝና ፀሃዩ ሳይገርር ልነሳ”
ወ/ሮ ማዘንጊያ ጉድ ጉድ ብለው ቁርስ አቀረቡና አብረው በልተው ተሰነባብተው ተለያዩ፡፡
አለቃ ቆላ ወርደው የታመመ ጠይቀው፣ የተጣሉትን ሁለት ሰዎች ሊያስታርቁ ግቢያቸው ሲደርሱ ጭራሽ ተጋግለው ቡጢ ሊቀማመሱ ግራ ቀኝ ሲሉ ያያሉ፡፡ ከሰዎቹ አንደኛው የተማረና አዋቂ የሚባል ነው፡፡
ሌላኛው ምንም ያልተማረና መሀይም ነው፡፡
መሀይሙ የተማረውን፡
“አንተ ደንቆሮ! ዶሮ ራስ!” ይለዋል፡፡
“አፍህን ዝጋ ነግሬሃለሁ!” ይላል የተማረው
“ደንቆሮ! ደደብ! ቆርቆሮ!” ይላል መሀይሙ፡፡
“ምንም ልሁን አፍህን ካልዘጋህ ዋጋህን ታገኛለህ!”
አለቃ፤
 “ተው እንጂ፤ ተው አይሆንም!” ይላሉ ሊገላግሉ መካከል ገብተው፡፡
መሀይሙ አሁንም፤ “ደንቆሮ! አለቃ፤ ይሄኮ ደደብ ነው!” ይላል፡፡
አለቃ፤ ሁለቱንም በተለያየ አቅጣጫ ገፍተው ይለያዩዋቸዋል፡፡
ይሄኔ አንድ መንገደኛ ድንገት ይደርሳል፡፡ አለቃ ያውቃቸዋል፡፡ ወደሳቸው ቀረብ ብሎ፤
“አለቃ ምን እያደረጉ ነው?” ሲል ይጠይቃቸዋል፡፡
አለቃም፤
“ስድብ ቦታውን ስቶብኝ፤ ቦታ ቦታው እየመለስኩ ነው!” አሉ፡፡
*   *   *
በሀገራችን ቦታውን የሳተ ብዙ ነገር አለ፡፡ ዲሞክራሲ ቦታውን ስቷል፡፡ ዲሞክራቱ አፉን ዘግቶ ተቀምጦ ሐሳዊ - ዲሞክራቱ ከጣራ በላይ ይጮሃል፡፡ የተማረው ፀጥ ብሎ መሀይሙ ያለ እ ኔ ማን አለ ይላል፡፡ “ምሁሩ ስፒከር ነገር የለው፣ መሀይሙ ባለ አምፕሊፋየር ነው፤” እንደተባለው ነው፤ ይሄ ክፉ እርግማን ነው፡፡
የሀገራችን ፀሐፌ ተውኔትና ገጣሚ ፀጋዬ ገ/መድህን፤
“ከመርገምት ሁሉ የከፋ መርገምት
ቋንቋ ለቋንቋ መጠፋፋት!”
ይለናል፡፡ ቋንቋ ለቋንቋ ከመጠፋፋት ይሰውረን፡፡ ቋንቋ ለቋንቋ ካልተደማመጥን፣ ቋንቋ  ለቋንቋ ካልተግባባን ለፍትሕ አንመችም፡፡ ቋንቋ ለቋንቋ ካልተናበብን ለሃይማኖት፣ ለጐሣ፣ ለእርስ በርስ ግጭት እንዳረጋለን፡፡
ተወያይተን መፍታት የምንችላቸውን ነገሮች፣ ተጋጭተን ወይም ተዋግተን ካልፈታን ብለን ያዙኝ ልቀቁኝ እንላለን፡፡ ከዚህ እርግማን ይሰውረን፡፡ አንድን ነገር ባንድ ጥሞና መፈፀም ሲገባን፣ ሁለት ሶስት ነገር ካልፈፀምን ብለን ስንራኮት አንዱንም ሳንጨብጥ እንቀራለን፡፡
“ራስ ሴላስ መስፍነ ኢትዮጵያ” የተባለው መጽሐፍ እንዲህ ይለናል፡-
“ዐባይን ከምንጩም ከመድረሻውም በአንድ ጊዜ ለመጨለፍ አይቻልም፡፡
የእናትየው አበባ ሳይረግፍ ልጅ እንቡጥ ትታቀፋለች፡፡ አባትየው ዓለምን ለመተው ዝግጁ ሳይሆን  ልጅ እውስጥ ገብቼ ልፈትፍት ይላል፡፡ በአንድ ጊዜ ደግሞ ለሁለት ትውልድ ቦታ የለም!”
አባት ታጋይ ቦታውን ለመልቀቅ ዝግጁ ሳይሆን ተተኪ ትውልድ ቦታውን ልውረስ ይላል እንደ
ማለት ነው፡፡ መተካካት ቀላል የማይሆነው ለዚህ ነው፡፡ ወጉ እንጂ ግብሩ ሩቅ ነው፡፡ የ60ዎቹ ዓመታት ታጋዮች (ዛሬ ያሉትን ያሸነፉትንም ጨምሮ) በየትኛውም መልኩ ተደራጅተው ይታገሉ የነበሩት ጊዜው የፈቀደውን ያህል ብስለት ነበራቸው፡፡ ትምህርቱ፣ ዕውቀቱ፣ ቅን ልቦናው ነበራቸው፡፡ ትግላቸው ዛሬ አቁሟል? ወይም ነገም ይቀጥላል? የትላንቱ ታሪክ የት ጋ ቆሞ አዲሱ ታሪክ የት ጋ ጀመረ? ታሪክ ተመራማሪዎች ይፈትሹት፡፡ አንድ ዕውነት ግን አለ፡፡ ዛሬ ሥልጣን ላይ ያለውን ፓርቲ ጨምሮ፣ ያ የዱሮው አስተሳሰብ ዛሬ፤ ሁሉም ላይ፣ ጥላውን ያጠላባቸዋል፡፡ የትግል ልምዳቸው ያው የትላንትናው ነው፡፡ “የነቃ፣ የተደራጀ፣ የታጠቀ ኃይል ያሸንፋል!” ነው የሁሉ ነገር መፍትሔያቸው፡፡ ለዚህ ሳይሆን አይቀርም፤ ዛሬ ቋንቋ ለቋንቋ መግባባት ያቃተው፡፡ ከንግግር ከውይይት ይልቅ ጦር መነቅነቅ ይቀናናል (Not the word but the sword እንደሚሉት ነው ፈረንጆቹ፡፡)
ያደግነው በህቡዕ ትግል (Clandestine Struggle) ውስጥ ነውና በሁሉም ወገን ያለን ፖለቲከኞች፤ በሰላም አገርን እናስብ ሲባል የባቢሎንን ግንብ እንደምንገነባ ሁሉ ቃል ለቃል መግባባት እርም ይሆንብናል፡፡ ፅንፍ መለየት (Polarization) ብቻ መፍትሄ ይመስለናል፡፡
ለሀገር ስንል ግማሽ መንገድ እንኳ አብረን እንሂድ መባባል ሽንፈት ይመስለናል፡፡ ገጣሚው እንዳለው፤ “ከዋሸህ ሽምጥጥ፤ ከመታህ ድርግም!” የሚል ፅንፈኛ መርህ ብቻ ሆኗል የሚገዛን! ትላንት ያልነውን ዛሬ ለመሻር ከቶም ዐይናችንን አናሽም፡፡ ለእለት ፖለቲካ እስከበጀን ድረስ መካድና መካካድ አይገደንም። ዋሽተን ማጣፊያው ሲያጥረን “ፖለቲካ እኮ ነው!” እንላለን፡፡ የመዋሸት ሊቼንሳ አለን እንደማለት፡፡ መንግስትም፣ ፓርቲም፣ ተቃዋሚም፣ ደጋፊም ይሄ ሊቼንሳ ያለው ነው የሚመስለው፡፡ አገር ያጠፋው አገር አለማሁ ይላል፡፡ ሙሰኛው የፀረ ሙስና ህግ አውጪ ይሆናል፡፡ ግፈኛው ስለ ፍትሕ ይሰብካል፡፡ መሀይሙ የተማረውን ቀጪ ተቆጪ ይሆናል፡፡ ቦታ ቦታው ያልተመለሰ አያሌ ወንጀለኛ በናጠጠባት አገር ዕድገት ማምጣት ከባድ ፈተና ነው፡፡ መንግሥት ይዋሻል ወይ? ሙሰኛ አለ ወይ? ፓርቲ ይሰርቃል ወይ? ወዘተ ብሎ የሚጠይቅ አይጠፋም፡፡ መልሱ፤ “አያ፤ የብሳና ዛፍ ይሸብታል ወይ?” ቢለው “ለዛፍ ሁሉ ያስተማረው ማን ሆነና ነው” አለው፤ የሚለው ተረት ነው፡፡

- አንድ የፓርላማ አባል በወር 10, 640 ዶላር ይከፈለዋል
- የግል ቤትና መኪና መግዣ የ257,400 ዶላር ብድር ይሰጠዋል
የኬንያ መንግስት የሰራተኞች ክፍያ ወጪውንለመቀነስ ሲል የፓርላማ አባላትን ወርሃዊ ደመወዝ  በ15 በመቶ ለመቀነስ ማቀዱን የዘገበው ቢቢሲ፤የአገሪቱ የፓርላማ አባላት ከፍተኛ ደመወዝ ከሚያገኙ የአለማችን ህግ አውጪዎች ተርታ ኬንያ የፓርላማ አባላትን ደመወዝ
በ15% ልትቀንስ ነው እንደሚሰለፉ ዘግቧል፡፡የኬንያ የፓርላማ አባላት በወር 7 ሺህ 200 ዶላር ደመወዝ ያገኙ እንደነበር ያስታወሰው
ዘገባው፤ የአገሪቱ መንግስት የያዘው አዲስ እቅድ ደመወዛቸውን በ15 በመቶ ከመቀነሱ በተጨማሪ፣በየሰበብ አስባቡ ያፍሱት የነበረውን ዳጎስ ያለ ውሎ አበልና ጥቅማጥቅም እንደሚያሳጣቸውም ገልጧል።አዲሱ ውሳኔ የመንግስት ባለስልጣናትን ደመወዝና ጥቅማጥቅሞች በከፍተኛ ሁኔታ
የሚቀንስ ነው ያለው ቢቢሲ፤ ከዚህ ቀደም የወር ደመወዛቸው ከ16 ሺህ ወደ 14 ሺህ ዶላር ዝቅ የተደረገባቸው የአገሪቱ ፕሬዚዳንትም በአዲሱ ህግ ሌላ ቅናሽ እንደሚደረግባቸው አመልክቷል፡፡በአገሪቱ አማካይ ወርሃዊ ገቢ 150 ዶላር ብቻ መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፤ የሚመለከተው የአገሪቱ ኮሚሽንም የሌሎች አገራትን ተሞክሮ በመገምገምና የፓርላማ አባላቱ ይህን ያህል ገንዘብ ማግኘታቸው አግባብ አለመሆኑን በማመን ቅናሽ እንዲደረግበት መወሰኑን ጠቅሶ፣ የደመወዝ ቅናሹም በመጪው ነሃሴ ወር መጀመሪያ የሚካሄደውን ብሄራዊ ምርጫ ተከትሎ ተግባራዊ ይደረጋል መባሉን አስረድቷል፡፡የኬንያ የፓርላማ አባላት ከ7 ሺህ 200 ዶላር ደመወዝ በተጨማሪ ከሚያገኙዋቸው ጥቅማጥቅሞች መካከልም፣ የ67 ሺህ 400 ዶላር የግል መኪና መግዣ ብድር፣ ለቤት መግዣ የሚውል የ190 ሺህ ዶላር ብድር፣ ለመንግስት ስራ የሚውል የ48 ሺህ ዶላር መኪና፣ እንዲሁም የ3 ሺህ 440 ዶላር ወርሃዊ የትራንስፖርትና የመኪና ጥገና ወጪ አበል እንደሚገኙበት ዘገባው ዘርዝሯል፡፡


    “ከግብር እና ከሞት ማንም አያመልጥም” ይሉ ነበር አሜሪካኖች፡፡ ቱጃሩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ደግሞ “ላወቀበት ብዙ መንገድ አለ” ይላሉ። የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሆነው ከመመረጣቸው በፊት የ916 ሚሊዮን ዶላር ኪሳራ እንዳጋጠማቸው በማሳየት ለ18 አመታት ያህል ይህ ነው የሚባል የፌደራል ታክስ እንዳልከፈሉ ይነገራል፡፡ ለአሜሪካ ፕሬዚዳንትነት በሚወዳደሩበት ወቅትም “የግብር ህጉን ክፍተቶች (loopholes) በመጠቀም አያሌ ረብጣዎችን ከግብር አድኛለሁ” ሲሉ በኩራት ተናግረዋል፡፡ “ችግሩ የኔ ሳይሆን የህጉና የህግ አውጭዎቹ ነው፡፡” በማለትም ጣታቸውን ወደ ተፎካካሪያቸው የቀድሞዋ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሒላሪ ክሊንተን ቀስረው ነበር፡፡ በመሰረቱ ግብር ማጭበርበር (tax evasion) እንጂ ከግብር ማምለጥ (tax avoidance) ወንጀል አይደለም፡፡
በግብር ጉዳይ በመንግስትና በዜጎች መካከል እሰጥ አገባዎችን ማየት አዲስ ነገር አይደለም፡፡ መንግስት ከግብር ብዙ ገቢ ለመሰብሰብ ሲጥር፣ ዜጎች በበኩላቸው፣ ከግብር ለማምለጥ ሲታትሩ፣ ማየት የተለመደ ነው፡፡ በግብር ጉዳይ በዜጎችና በመንግስት መካከል በሚፈጠር አለመግባባት ብዙ ዙፋኖች ተነቃንቀዋል፡፡ ትላልቅ ግዛቶች (empires) ወድቀዋል፡፡ ለግብፅ፣ ለሮምና ለስፔን ሰፋሪ ግዛቶች (empires) መፍረስ አንዱ ምክንያት በግብር ምክንያት የተቀሰቀሱ አመፆች እንደሆኑ ይነገራል።
ብሪታኒያ ከአትላንቲክ ማዶ ካለው ሰፊው ርስቷ የተቀነሰችው፣ የአሜሪካም አብዮት የፈነዳው በግብር ምክንያት በተፈጠረ እሰጥ አገባ መሆኑን ታሪክ ይመሰክራል፡፡ በስኳር ላይ የተጣለው ግብር፣ የቴምብር ቀረጥና በሻይ ላይ የተጣለው ታክስ በአሜሪካ ይኖሩ የነበሩትን ሰፋሪዎች አስቆጣ፡፡ በእንግሊዝ ፓርላማ ውስጥ ሳንወከል በሚወጡ የግብር ህጎች መገዛት የለብንም (No taxation without representation) አሉ፡፡ በዚህ ሰበብ የተለኮሰው የአመፅ እሳት፤ ብሪታኒያን አንገብግቦ አስወጣት፤ ሰፋሪዎቹም ነፃ የአሜሪካን መንግስት መሰረቱ፡፡
የፈረንሳይ አብዮትም የፈነዳው ሀገሪቷ የተቆለለባትን ግዙፍ ዕዳ ለመክፈል ዜጎቿ ላይ የጫነችው እጅግ የበዛ ግብር የህዝቡን ቁጣ በመቀስቀሱ ነው፡፡ ከበርቴው ከግብር ነፃ ሲሆን፣ ገበሬውና የሰራተኛው መደብ በተጫነባቸው ከፍተኛ ግብር ክፉኛ ማቅቀዋል፡፡ ይህ ፍትሐዊነት የጎደለው የግብር ስርዓት፤ የፈረንሳይን አብዮት አስነስቶ፣ ሉዊስ 16ኛም ስልጣኑን ብቻ ሳይሆን ህይወቱን አጣ፡፡ ለእንግሊዝ አብዮት አንዱ መነሻም በግብር ምክንያት የተነሳ ብሶት ነው፡፡
በተለያዩ ጊዜያት በግብር ምክንያት በርካታ ንትርኮችና አለመግባባቶች በመንግስትና በዜጎች መካከል ተፈጥረዋል፡፡ ሰሞኑን በመዲናችን አዲስ አበባ በደረጃ “ሐ” ግብር ከፋዮች የሚሰማው ብሶት አንዱ ማሳያ ነው፡፡ የደረጃ “ሐ” ግብር ከፋዮች የግብር ግዴታቸውን የሚወጡት የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን (ኢገጉባ) በቀን ገቢ ላይ ተመስርቶ በሚወስነው የገንዘብ መጠን ነው፡፡ ይህ በግምት ላይ ተመስርቶ የሚከፈል የደረጃ “ሐ” ግብር፣ የአፈፃፀም ችግሮች ብቻ ሳይሆን ይህን ለመወሰን የመጡት የግብር ህጎችም የራሳቸው ክፍተቶች አሉባቸው፡፡
በተሻሻለው የግብር አዋጁ መሰረት የደረጃ “ሐ” ግብር ከፋይ ማለት አመታዊ ጠቅላላ ገቢያቸው ከ500 ሺህ ብር በታች የሆኑ ግለሰቦች ናቸው፡፡ የትኛውንም ያህል መጠን የሚያገኙ ድርጅቶች ግን እንደ ደረጃ “ሀ” ግብር ከፋይ ይቆጠራሉ፡፡ በቀድሞው የግብር አዋጅ ደረጃ “ሐ” ግብር ከፋይ ማለት አመታዊ ገቢያቸው ከ100 ሺህ በታች የነበሩት ናቸው፡፡ የደረጃ “ሐ” ግብር ከፋዮች ግብር የሚከፍሉት አማካይ የቀን ገቢያቸው ተገምቶ፣ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን (ኢገጉባ) ባስቀመጠው ቀመር መሰረት ነው፡፡ ደረጃ “ሐ” ለግብር አሰቸጋሪ (hard - to - tax) የሚሆኑ የስራ ዘርፎች የተሰባሰቡበት መደብ ነው፡፡ በዚህ መደብ ላይ የጣለው ግብር ምንጊዜም ከውዝግብ ርቆ አያውቅም፡፡
ከዚህ መደብ ሥር ያሉ ግብር ከፋዮችን የሒሳብ መዝገብ እንዲይዙ ማድረግ ለግብር ከፋዮቿም ሆነ መንግስት ግብርን ለመሠብሠብ የሚያደርገውን ወጪ በእጅጉ ያበዛዋል፡፡ ለዚህም ነው በቀን ገቢ ግምት ላይ የተመሠረተ ግብር እንዲከፍሉ የሚደረገው፡፡ ይህ ሆኖ ሳለ ይህን ግብር ለማስፈፀም የወጡት አዲሱ የገቢ ግብር ደንብ ሠንጠረዥም ሆነ መመሪያ ቁጥር 123/2009 ችግሮች ይታዩባቸዋል፡፡ ለተፈጠረው የትመና ችግርም የየራሳቸውን ድርሻ አበርክተዋል፡፡
የአዲሡን የግብር አዋጅ መውጣት ተከትሎ፣ አዲስ የግብር ደንብ ተረቅቆ በዚህ ወር ይወጣል ተብሎ ይገመታል፡፡ ይህ ረቂቅ ደንብ ደረጃ ‹‹ሐ›› ግብር ከፋዮች የተሰማሩባቸውን የንግድ ዘርፎች ይዘረዝራል፡፡ ይህ ሠንጠረዥ ከጌሾና ብቅል ንግድ ጀምሮ እስከ ጀበና ቡና ንግድ ድረስ በአጠቃላይ ዘጠና ዘጠኝ የንግድ ዘርፎችን አካቶ ይዟል፡፡
ይህ ዝርዝር በሃገሪቱ ውስጥ ብሎም በአዲስ አበባ ውስጥ የሚከናወኑ የንግድ ሥራዎችን ያጠቃልላል ብሎ ማሠብ አይቻልም፡፡ ይህ የግብር ሰንጠረዥ የንግድ ሚኒስቴር ከተዘጋጀው የንግድ ፈቃድና የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ለመስጠት ከሚጠቀምበት የንግድ ስራ ፍቃድ መስጫ መደቦች መመሪያ (Ethiopian standard industrial classification) ጋር ቢጣጣም የተሻለ ይሆን ነበር፡፡ ይህ የንግድ ሥራ ፍቃድ መስጫ መደቦች መመሪያ የራሡ የሆኑ ክፍተቶች ቢኖሩትም፣ ከሞላ ጎደል በሃገሪቱ ውስጥ የሚከናወኑ የንግድ ስራዎችን ያካተተ ነው፡፡ ይህ ካልሆነ ግን በግብር ደንቡ ባለው ሠንጠረዥ ላይ ብቻ ተመስርቶ የደረጃ ‹‹ሐ›› ግብርን መሠብሰብ ብዙ ችግሮችን ያስከትላል፡፡
ደረጃ ‹‹ሐ›› ግብር ከፋዮች የሚከፍሉት የግብር  መጠን የሚወሠነው የግብር ከፋዩን የቀን ገቢ መጠን ሊያሳዩ የሚችሉ አመላካቾችን (indicators) በመጠቀም ነው፡፡ ነገር ግን እነዚህ አመለካከቶች (indicators) ሙሉ ለሙሉ ተጨባጭ (objective) ናቸው ማለት አይቻልም። የግብር ሰብሳቢ መስሪያ ቤት የሚጠቀምባቸው መለኪያዎች ሙሉ ለሙሉ ተጨባጭ ካለመሆናቸው በተጨማሪ ገቢ በመገመት ሂደቱ ላይ የገማቾች የተለያየ ህላዓዊ ፍርድ (Subjectivity) ሲታከልበት በተመሳሳይ ሁኔታ ላይ ያሉ ግብር ከፋዮች የተለያዩ መጠን ያለው ግብር እንዲከፍሉ ይገደዳሉ፡፡ ይህ የቀን ገቢ መጠን ላይ የተመሠረተ ግብር በተቻለ መጠን ህሊናዊ ፍርድን (Subjectivity) እስካላስቀረ ድረስ እና ሳይንሳዊነትን እስካልተላበሠ ድረስ ኢ-ፍትሐዊ (in-equitable) ግብር መኖሩ አይቀሬ ነው፡፡
ችግሩን የከፋ ያደረገው ደግሞ አዲስ አበባ ላይ የቀን ገቢ ላይ የተመሠረተ ግብር ትመና የተካሔደው ከስድስት አመታት በፊት 2003 ዓ.ም ላይ ነው፡፡ በነዚህ ስድስት አመታት ውስጥ የገቢያቸው መጠን የጨመረ የሚጠበቅባቸውን ግብር ሳይከፍሉ፣ የገቢያቸው መጠን ያሽቆለቆለ ግብር ከፋዮች በበኩላቸው፤ ያልተገባ ግብር ሲከፍሉ ኖረዋል፡፡ ‹‹ጭራሽ ከመቅረት ዘግይቶ መድረስ ይሻላል›› እንደሚባለው፤ ከስድስት አመታት በኋላም ቢሆን የግብር ክለሳ መካሔዱም አንድ ነገር ነው፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያ ጉምሩክ ባለስልጣን፤ በትመና ሥራው ላይ የተሠማሩ ሰዎችን በዘመቻ ካሠለጠነ በኋላ የትመና ሥራውንም በዘመቻ እንዲሠሩ ማድረጉ፣ እውነተኛ ገቢን እንዲሁም ግብርን ማንፀባረቅ አለመቻሉ፤ ቅሬታንም መፍጠሩ የሚያስገርም አይደለም፡፡
የደረጃ ‹‹ሐ›› ግብ ከፋዮች የሒሳብ መዝገብ በመያዝ የተወሰነባቸውን የቀን ገቢ እንዲሁም በዚያ ላይ የተጣለውን ግብር የማስቀየር (rebut) የማድረግ ዕድሉ በህግ ተደንግጎ ቢሠጣቸው ችግሩን በተወሠነ መልኩም ቢሆን መቀነስ ይቻላል፡፡ እንዲህ አይነት ዕድል የደረጃ ‹‹ሐ›› ግብር ከፋይን የሒሳብ መዝገብ እንዲይዝ ያበረታታዋል፡፡ የያዙትን የሒሳብ መዝገብም በማየት ከደረጃ ‹‹ሐ›› ወደ ደረጃ ‹‹ለ›› እና ደረጃ ‹‹ሀ›› የተሸጋገሩ ግብር ከፋዮችን በቀላሉና በማያሻማ ሁኔታ መለየት ይቻላል፡፡ በአሁን ሰአት በደረጃ ‹‹ሐ›› ያሉ ግብር ከፋዮች ወደ ሌሎች የግብር ደረጃዎች መሸጋገራቸውን ግብር ሠብሣቢው መሥሪያ ቤት እንዴት እንደሚመዝን ማሠብ በራሡ ትልቅ ጥያቄ ያጭራል፡፡
ግብርን መደበቅ፣ በገቢ ትመና ወቅትም እቃዎችን መሰወር፣ ህፃናትን በሱቆች ላይ አስቀምጦ መሔድ፣ ሱቅ ዘግቶ መጥፋት እና የመሣሠሉት ችግሮች የሚፈጠሩት በግብር ከፋይ ዘንድ የግብርን ጥቅም ካለመገንዘብ በተጨማሪ ፍትሐዊ ያልሆነ ግብር መጫኑ ሌላው ምክንያት ነው፡፡ ተገቢነት የሌለውን ከፍተኛ ግብር በመፍራት ሱቁን ዘግቶ ቢጠፋ ምንም አያስገርምም፡፡
በገቢ ግብር ደንቡ ሠንጠረዥ ላይ የተቀመጠው አማካይ የትርፍ (Profitability rate) መቶኛ  በራሱ እንዴት እንደተወሠነ ግራ አጋቢ ነው፡፡ በሠንጠረዡ ላይ ያሉ የንግድ ዘርፎች አይከስሩም የማለት አንድታም ያለው ይመስላል፡፡ በደረጃ ‹‹ሐ›› ሥር ያሉ ግብር ከፋዮች እንደማንኛውም ነጋዴ የሚያጋጥማቸውን ትርፍም ሆነ ኪሣራ የረሳው ይመስላል፡፡
ይልቁንም በዚህ መደብ ያሉ አነስተኛ ግብር ከፋዮች የገጠማቸውን ኪሣራ በሒሳብ መዝገብ የሚያስረዱበት እድል ቢፈጠርላቸው፣ ኪሣራቸውንም እንዲያሸጋግሩ ቢፈቀድላቸው በርካታ የደረጃ ‹‹ሐ›› ግብር ከፋዮች የሒሳብ መዝገብ በመያዝ፤ አሁን የተፈጠረውን ችግር መቀነስ ይቻላል፡፡ መንግስት ከአፈፃፀም ችግሮች በተጨማሪ የህጉንም ግድፈቶች በማየት የግብር ከፋዩን ቅሬታ ሊፈታ ይገባል፡፡