Administrator

Administrator

Monday, 25 September 2017 11:56

የዒላማ ግርዶሽ

ርዕስ የለሽ ጽሕፈት
ውል አልባ ምዕራፍ
የምገርፈው በሬ
የሚጮኸው ጅራፍ
ያገር ደጅ ስጠና
ተከፈተ በራፍ፡፡
ክፋት ላይ ስተኩስ
ቅንነት ተመታች
ለተኩላ ባለምኩት
እርግብ በ’ራ ገባች
እርኩስ መቺ ቀስቴ
ደግ ላይ ተሰካች፡፡
ባላሚ ታላሚ
መሀል ስቶ ገብቶ
የዒላማ ግርዶሽ
ባገር ተንሰራፍቶ
አልሞ ለመምታት
አልተቻለም ከቶ፡፡
ከምሥጋና ጋር
ሳምሶን ጌታቸው ተ/ሥላሴ

* የቅዱስ ላሊበላ ደብርንና የደብረ ሊባኖስ ገዳምን ይጐበኛሉ
* ከፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ ጋር እንደሚነጋገሩ ይጠበቃል

     የሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ቅዱስ ባስልዮስ ማር ቶማ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ የፊታችን ማክሰኞ በሚከበረው የመስቀል ደመራ በዓል ላይ ለመገኘት ከነገ በስቲያ ቀትር ላይ አዲስ አበባ የሚገቡ ሲሆን ከርእሰ ብሔሩ ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ ጋራ ተገናኝተው እንደሚነጋገሩ ተጠቁሟል፡፡
ቅዱስ ፓትርያርኩ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን አምስት ልኡካን በመምራትም፣ በኢትዮጵያ የአራት ቀናት ጉብኝት እንደሚያደርጉ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡
ለጉብኝቱ በወጣው መርሐ ግብር መሠረት፥ ሰኞ፣ ከቀትር በኋላ፣ የህንዱ ፓትርያርክ፣ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ኦፌሴላዊ አቀባበል ይደረግላቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱና የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ሊቃውንት፣ የሰንበት ት/ቤት አባላትና ምእመናን በተገኙበት በሚደረገው አቀባበል፣ ፓትርያርኩ፣ ትምህርተ ወንጌል ይሰጣሉ፤ ተብሏል፡፡
በማግሥቱ ማክሰኞ፣ ከርእሰ ብሔሩ ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ ጋራ ተገናኝተው እንደሚነጋገሩ የተጠቀሰ ሲሆን፤ ከቀትር በኋላም፣ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ጋራ ወደ መስቀል ዐደባባይ በማምራት፣ የደመራን በዓል ያከብራሉ፡፡ ብዙ ሺሕ የሰንበት ት/ቤቶች ወጣቶች የሚያቀርቡትንና የሥነ በዓሉ ድምቀት የሆነውን ዐውደ ትርኢት የሚመለከቱት የህንዱ ፓትርያርክ፤ የሁለቱን አገሮችና አብያተ ክርስቲያናት ጥንታዊ ወዳጅነትና ቀጣይ ግንኙነት የተመለከተ ንግግር የሚያደርጉ ሲሆን ደመራውን፣ ከፓትርያርክ አቡነ ማትያስና ከአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ድሪባ ኩማ ጋራ በአንድነት እንደሚለኩሱ ተጠቁሟል፡፡
በዕለተ ረቡዕ የመስቀል በዓልን፣ በላሊበላ ደብር ውቅር አብያተ ክርስቲያናት በመገኘት እንደሚያከብሩም የተገለጸ ሲሆን ከዚያም መልስ፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ቤተ መጻሕፍት ወመዘክርን፣ የሰበታ ጌቴሰማኔ ቤተ ደናግል ሴቶች ገዳምንና የደብረ ሊባኖስ ገዳምን እንደሚጎበኙ መርሐ ግብሩ ያስረዳል። ከጉብኝታቸው ፍጻሜ በኋላ፣ በሁለቱ እኅትማማች አብያተ ክርስቲያናት አንድነትና ዓለም አቀፍ አገልግሎት ዙሪያ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ ደረጃ የጋራ ምክክር እንደሚያካሒዱና መግለጫም እንደሚሰጡ ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ ባለፈው ዓመት ኅዳር ሕንድን በጎበኙበት ወቅት ባቀረቡላቸው ግብዣ መሠረት፣ መስቀል ደመራን በኢትዮጵያ የሚያከብሩት ቅዱስ ባስልዮስ ማር ቶማ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ ለመጀመሪያ ጊዜ ከተገኙበት የካቲት ወር 2005 ዓ.ም. በዓለ ሢመት ወዲህ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ የሚያደርጉት ጉብኝት እንደሆነና የሁለቱን አብያተ ክርስቲያናት የተጠናከረ ግንኙነት እንደሚያሳይ ተጠቅሷል፡፡
ከቀድሞም ጀምሮ በአገራችን ዘመናዊ ትምህርት ቤቶች ጎልቶ የሚታየው የሕንዳውያን መምህራን አገልግሎት፣ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሥነ መለኰት ኮሌጆችም መኖሩን ምንጮቹ አስገንዝበዋል፡፡ በአንጋፋው የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በማስተማር የሚታወቁ ዕውቅ የሥነ መለኰት ሊቃውንትን ያወሱት ምንጮቹ፤ ኮሌጁ በቀድሞው መንግሥት ተዘግቶ ዳግም ከተከፈተበት ከ1987 ዓ.ም. ወዲህም አገልግሎታቸው መቀጠሉንና ከመምህራኑም  መካከል ለማዕርገ ጵጵስና የበቁ እንዳሉ ጠቅሰዋል። ይህም፣ የቆየውን ግንኙነትና ትብብር ለማጠናከር ከፍተኛ ሚና መጫወቱን አስረድተዋል፡፡
ቅዱስ ባስልዮስ ማር ቶማ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ እ.ኤ.አ ከኖቨምበር 2010 ጀምሮ፣ በሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ቶማስ የተሠየሙ 91ኛው የምሥራቅ ካቶሊኮስና የማላንካራ መጥሮጶሊጣን ናቸው፡፡ በኦፊሴላዊ ስያሜዋ፣ የማላንካራ ኦርቶዶክስ ሶርያ ቤተ ክርስቲያን ወይም የኦርቶዶክስ ሶርያዊ ምሥራቅ ቤተ ክርስቲያን ተብላ የምትጠራው የሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን፣ በሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ በ52 ዓ.ም. የተመሠረተች ጥንታዊት ናት፡፡ በደቡብ ሕንድ የምትገኘው ኬሬላ ወይም ማላንካራ፣ የክርስትናው መሠረት የተጣለባት የመንበሩ መቀመጫ ስትሆን፤ ካቶሊኮስ የሚለው የርእሰ መንበሩ ሥያሜም የፓትርያርክ አቻ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ በአሁኑ ወቅት ቤተ ክርስቲያኒቱ፣ በሊቃነ ጳጳሳት የሚመሩ 25 የሀገር ውስጥና የውጭ አህጉረ ስብከትን እንዳቋቋመችና ከ2.5 ሚሊዮን በላይ ተከታዮች እንዳሏት መረጃዎች ያሳያሉ፡፡
በሌላ በኩል፣ ትውልደ ሕንዳውያንና የኦርቶዶክስ ክርስትና ተከታይ የሆኑ በርካታ ተሳላሚዎች፣ የሕንዱን ፓትርያርክ በመከተል በአዲስ አበባ የመስቀል ዐደባባይ ተገኝተው የደመራን በዓል እንደሚያከብሩ ታውቋል። ነዋሪነታቸውን በሕንድ፣ በአሜሪካና በእስራኤል ያደረጉ መነኰሳትን፣ ካህናትንና ምእመናንን ያካተተውና በአርባ አምስት ቡድን የተደራጀው ይኸው የተሳላሚዎቹ መንፈሳዊ ጉዞ፣ በአንጋፋው የሙምባዩ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ የሚመራ እንደሆነ ተነግሯል፡፡ የጠቅላይ ጽ/ቤቱ ምንጮች እንደገለጹት፣ ተሳላሚዎቹ፣ “በኢትዮጵያ ገዳማት ሥርዓትና አኗኗር ዝና ተስበው የመጡ መንፈሳውያን ተጓዦች ናቸው፡፡” በኒውዴልሂ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቢሮ አስተባባሪነት በተዘጋጀው ጉብኝት ፓኬጅ መሠረትም፣ የደመራን በዓል በመስቀል ዐደባባይ ተገኝተው ያከብራሉ፤ የላሊበላ ደብር ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን፣ የጣና ገዳማትንና የጠቅላይ ጽ/ቤቱን ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር ይጎበኛሉ፤ ብለዋል - ምንጮቹ፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንድ እናት ቢምቢ ትንኝና ልጅ ቢንቢ ትንኝ ነበሩ፡፡ ልጅዬዋ ቢምቢ፤ በአገሩ እየተዘዋወረች ዙሪያ ገባው ውስጥ ነዋሪ - የሆኑትን እንስሳት፣ አዕዋፍና ነብሳት ልትጠይቃቸው ጎራ ልትል አሰበች፡፡ ይህንን ያወቀችው እናት፤
“መሄዱንስ ሂጂ፡፡ ዘመድ ማግኘትና መጠየቅ በጣም ጥሩ ነው፡፡ ነገር ግን ወዳጅና ጠላትሽን መለየት ይኖርብሻል፡፡ ጠላት የመሰለሽ ወዳጅ ሆኖ ይገኛል፡፡ ወዳጅ ያልሺው ደግሞ፣ ጠላት ሆኖ ተለውጦ ታገኚዋለሽ። ለማንኛውም ማጣራትን የመሰለ ነገር የለም፡፡”
ልጅዬዋ ቢምቢም፤
“እሺ እማማ፣ ቀስ ብዬ እያጣራሁ ለማየት እሞክራለሁ” ብላ አካባቢዋን ልታጠና መንገድ ቀጠለች፡፡
መጀመሪያ ቢራቢሮን አገኘች፡፡ “ቢራቢሮ እንደምነሽ?”
ቢራቢሮ፤
“ደህና ነኝ” አለች፡፡
“በአካባቢው ያሉ ነብሳት ተስማምተውሽ ይኖራሉ?”
“አዎን፡፡ ግን ክረምትም በጋም ሳልቸገር ለመኖር በመቻሌ፣ ወረተኛ ነሽ እያሉ ይወቅሱኛል”
“እነሱ ምን ፈልገው ነው?”
“ወይ የበጋ ሁኚ ወይ የክረምት ሁኚ ነው የሚሉኝ”
“ቆይ፤ ስለዚህ ጉዳይ እናቴን ጠይቄ ምን እንደምትል እነግርሻለሁ” ብላት ቢምቢ ሄደች፡፡
ቀጥላ ጦጣን አገኘቻት፡፡
“ጦጢት እንደምንድነሽ?”
“ደህና ነኝ”
“ከእንስሳቱ ጋር ስትኖሪ ምን ችግር ገጥሞሽ ያውቃል?”
“ምንም ችግር አልገጠመኝም፡፡ ግን ሁሉም በአንድነት በእኔ ላይ ፈርደው ብልጣ - ብልጥ ብትሆኚ ምን አለበት ታዲያ?”
“ታታልይኛለሽ፡፡ ታሞኚኛለሽ እያሉ ነው፡፡”
“የራሳቸው ጅልነት ነው ተያቸው” ብላ ቢምቢ መንገድ ትቀጥላለች፡፡
ብዙም ሳትሄድ አንበሳን አገኘችው፡፡
ቢምቢ፤
“ደህና ዋልክ አያ አንበሶ?”
“ደህና ነኝ፤ ቢምቢ”
“እንስሳት አብረውህ ሲኖሩ ምን ይሉሃል?”
“ጉልበተኛ ነህ፡፡ አምባገነን ነህ፤ ነው የሚሉኝ” አለ እየተጎማለለ፡፡
“አቅም ስላነሳቸው ነው እነሱ፡፡ ተዋቸው፡፡” ብላው መንገዷን ቀጠለች፡፡
በመጨረሻ የተሰበሰቡ ሰዎች አግኝታ፣ እነሱን አዳመጠችና፣ እየመሸ ስለመጣ ወደ እናቷ ተመለሰች፡፡
የሆነችውን ሁሉ ነገረቻት፡፡
“ሰዎችስ ምን አሉሽ?” አለቻት እናት ቢምቢ፡፡
ልጅየዋ ቢምቢም፤
“ይገርምሻል፤ ሰዎችማ ሲያጨበጭቡልኝ ዋሉ” አለቻት፡፡
እናት ቢምቢም፤
“ልጄ ሁለተኛ እንዳትሳሳቺ! እንደ፣ሰዎች ክፉ የለም፡፡ ያጨበጨቡልሽ የመሰለሽም በመዳፍና መዳፋቸው ጨፍልቀው ሊገድሉሽ ሲሞክሩ ነው፡፡ ስለዚህ ዳግመኛ እንዳትታለይላቸው!” አለችና መከረቻት፡- “ማጨብጨብ የሰው ልጆች ኃይለኛ መሳሪያ ነው፤ ተጠንቀቂ!”
*           *           *
አክራሪ መሆን መጥፎ የመሆኑን ያህል አድር - ባይና ወላዋይ መሆንም ያንኑ ያህል አስቸጋሪ ጠባይ ነው! ብልጣ ብልጥ መሆን የራሱ ችግር እንዳለው ሁሉ፣ ሞኛ - ሞኝ መሆንም ለማንም ብልጥ - ነኝ - ባይ የማታለል ተግባር ሰለባ ስለሚያደርግ፤ መጠንቀቅ ተገቢ ነው! አምባገነንነት ሁልጊዜ አያበላም፡፡ በእርግጥም የተገፉ፣ የተበደሉ፣ ፍትሕ - ያጡ፣ የተመረሩ ህዝቦች በተነሱ ጊዜ ማናቸውም ፈላጭ - ቆራጭ አገዛዝ አሳሩን ያያል፡፡ በዓለም ላይ ስንት አምባገነኖች ተሰባብረው እንደወደቁ ማሰላሰል ነው! የደገፉ መስለው ጧት ማታ ሲያጨበጭቡልን ጤነኛ መስለውን፤ “አሁን ነው ራስን ማሳየት” ብሎ ብቅ ማለት አደጋ አለው! ለመውረድ ብዙ ሽቅብ መውጣትም ክፉ ባህሪ ነው፡፡ ሁሉን፣ ሁልጊዜ አገኛለሁ ማለትም ግብዝነት ነው፡፡ እያጨበጨቡ ጎል ከሚከቱን ይሰውረን!
ዛሬ የትምህርት ጊዜ ነውና ትምህርታችንን ይግለጥልን፡፡ እንደ እስያ፤ “ዕውቀት እያለ የሚማር ጠፋብን” የሚል ትራጀዲ ውስጥ እንዳንገባ አምላክ ይጠብቀን!
“ምዕራቡ ዓለም ሲያስነጥስ ሌላው ክፍለ ዓለም ኒሞኒያ ይይዘዋል” የሚለውን በማሰብ፤ እንዳይምታታብን ራሳችንን እንቻል! የራስን የመሰለ ምንም ነገር የለም፡፡
የመጨረሻው እንግሊዛዊ የህንድ ገዢ ሎርድ ሉዊ፣ ለማህታማ ጋንዲ እንዲህ አለው “እኛ ከወጣን በህንድ አገር ቀውስ ይፈጠራል!”
ይሄኔ ማህታማ ጋንዲ፤
“አዎን ቀውስ ይፈጠራል - ቀውሱ ግን የራሳችን ነው!” አለና፤ ኩም አደረገው፡፡
“የራሳችንን ቀውስ ‘ራሳችን እንፈታዋለን!”
አንድ ፀሐፊ ካነበብናቸው በርካታ መጣጥፎች አንዱ ላይ፤ “የአዕምሯችን ማዕከል፣ እና ደጃፉም ሆነ ግንባሩ በጣም ሩቅ ለሩቅ ናቸው! ግን ተቀናጅተው ሥራ ይሰራሉ” ይላል፡፡ የእኛም ተግባር እንደዚሁ የተቀናጀ መሆን ይኖርበታል! ከተሳሰብንና ከተናበብን የስሌት ስህተት አንሰራም፡፡ የፍርድ ማዛባት ስህተት አንሰራም፡፡ የመረዳዳት ማቃት ስህተት አንሰራም፡፡
ዛሬ “ነፃ ኢኮኖሚ”፣ “ዲሞክራሲ”፣ “መልካም አስተዳደር” አስፈላጊ ነው ብለን ተፈጥመናል፡፡ ያም ሆኖ የፌደራሊዝምን ስርዓት፣ በተለይ የብሔር ብሔረሰብን ፌደራሊዝም ጨርሶ ካላደገው ካፒታሊዝማችን ጋር አብረን ለማስኬድ ብዙ እንቅፋት ሲፈጠርብን ይታያል፡፡ ኦሊቨር ጎልድስሚዝ የተባለው ገጣሚ፤ “ሀብት ይከማቻል ሰው ይበሰብሳል” ወደ ውስጥ እያየን፣ ራሳችንን እንፈትሽ፡፡ ነፃ ኢኮኖሚ ስንል በምን የዕድገት ደረጃ ላይ ላለ ኢኮኖሚ ነው ያጨነው? ብለን እንጠይቅ፡፡ ዲሞክራሲ ስንል በምን ደረጃ ላለ አገር ነው ያስቀደድነውና ስፌቱን የምንመርጠው? እንበል፡፡ ከፊውዶ ቡርዥዋ ሥርዓት ገና ሙሉ ለሙሉ ባልተላቀቀ ፖለቲካል-ኢኮኖሚ ላይ መልካም አስተዳደርን መጋለብ ቀርቶ መፈናጠጥስ ይቻላል ወይ? ብለን እንጠይቅ! ታላቅ ኃይል ያዘለውን ካፒታሊዝም፤ ከማህበረሰባዊ ኮንሰርቫቲዝም ጋር ማጋባትስ አማራጭ ይሆናል ወይ? (ምናልባት የቻይናን፣ የህንድን ስነልቦና ቢሰጠን) ብለን እንመርምር፡፡
የንድፈ-ሀሳብ መንገዳችን ከረኮንች ነው፡፡ እንኳንስ አስፋልት ኮብል-ስቶኑም ገና እያንገዳገደን ነው፡፡ ቆም ብሎ የሚያስብ አስተዋይ አዕምሮ አሁንም ያስፈልገናል! ከዕለታት አንድ ቀን የያዝነው ቲዎሪ ስህተት ሆኖ ቢሆንስ? ብለን መጠያየቅ አይከፋም፡፡ ለሁሉም ህመም አንድ መድኃኒት በመስጠት (ፓናሲያ እንዲሉ) ፈውስ እናገኛለን ብሎ ማሰብ ቀቢፀ- ተስፋ ነው፡፡ ማርክ ትዌይን፤ “መዶሻ ያለው ሰው፣ እያንዳንዱ ችግር ሚሥማር ይመስለዋል!” የሚለው በእኛ ዓይነቱ ላይ ሲሳለቅ ነው፡፡ ከዚህም ይሰውረን፡፡
ለክርስትና ዕምነት ተከታዮች መልካም የመስቀል በዓል!  

      ሚዩዚክ ሜይዴይ ከኢትዮጵስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር፣ ነገ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ በብሄራዊ ቤተ መፃህፍትና ቤተመዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ፣ በአለቃ ዘነበ እና በአለቃ ወልደማሪያም በተፃፉ የአፄ ቴዎድሮስ ዜና መዋዕሎች ላይ ውይይት ያካሂዳል፡፡ ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት ገጣሚና ደራሲ ይታገሱ ጌትነት ሲሆን በዝግጅቱ ላይ ለመሳተፍ ፍላጎት ያለው ሁሉ እንዲሳተፍ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ጋብዟል፡፡

ባለፈው ሰኞ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት አዲስ ማዕቀብ የተጣለባት ሰሜን ኮርያ፣ ይህ ማዕቀብ እንዲጣልብኝ ቁልፍ ሚና ተጫውተዋልና እቀጣቸዋለሁ በሚል፣ “ጃፓንን በውሃ ማዕበል አሰምጣለሁ፣ አሜሪካን ደግሞ ዶግ አመድ አደርጋለሁ” ስትል መዛቷን ዘ ጋርዲያን ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት፣ በቅርቡ ካደረገቺው የኒውክሌር ሙከራ ጋር በተያያዘ በሰሜን ኮርያ ላይ ባለፈው ሰኞ አዲስ ማዕቀብ መጣሉን ያስታወሰው ዘገባው፤ የአገሪቱ መንግስት የውጭ ግንኙነት ኮሚሽንም ይህን አድርጋለች በሚል በአሜሪካ ላይ ከተለመደው በተለየ መልኩ ጠንከር ያለና ብዙዎችን ያነጋገረ ዛቻ መሰንዘሩን ገልጧል፡፡
የሰሜን ኮርያ መንግስት የዜና ወኪል ሃሙስ ዕለት ባሰራጨው ዘገባ፤ የሰሜን ኮርያ መንግስት አራት የጃፓን ደሴቶችን በኒውክሌር ቦንብ ጥቃት ውሃ ውስጥ እንደሚያሰምጥና አሜሪካንም በከፍተኛ ጥቃት ዶግ አመድ እንደሚያደርግ አስታውቋል፡፡
ይህን ተከትሎ የጃፓን መንግስት ቃል አቀባይ፣ የሰሜን ኮርያን ዛቻ “ጸብ አጫሪና እጅግ አደገኛ” በሚል ማውገዛቸውንና ዛቻው በአካባቢው ያለውን ውጥረት የሚያባብስና ተቀባይነት የሌለው ነው በሚል ማጣጣላቸውንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡
ዘ ኢንዲፔንደንት በበኩሉ፣ 15 አባላት ያሉት የተመድ የጸጥታው ምክር ቤት፣ ሰሜን ኮርያ የጨርቃ ጨርቅ ምርቶችን ወደ ውጭ አገራት እንዳትልክ የሚከለክለውንና በአሜሪካ የረቀቀውን የማዕቀብ ሃሳብ ባለፈው ሰኞ ማጽደቁ በአካባቢው ያለውን ውጥረት የበለጠ እንዳባባሰው ዘግቧል፡

 ሳምሰንግ በመሪነቱ ሲቀጥል፣ አፕል ወደ 3ኛ ደረጃ ዝቅ ብሏል

     የቻይናው የቴሌኮም ኩባንያ ሁዋዌ፣ አይፎንን በሚያመርተው የአሜሪካው አፕል ለዓመታት ተይዞ የነበረውን የአለማችን የስማርት ፎን ሽያጭ የሁለተኛነት ደረጃ መረከቡን የእንግሊዙ ቴሌግራፍ ዘግቧል፡፡
ሁዋዌ ባለፉት ሰኔ እና ሐምሌ ወራት ያስመዘገበው የስማርት ፎን ሽያጭ ከአፕል ብልጫ በማሳየት ወደ ሁለተኛነት ደረጃ ከፍ ማለቱን ከሰሞኑ ይፋ የተደረገን የገበያ ጥናት ጠቅሶ ያመለከተው ዘገባው፤ ይህም ሆኖ ግን አፕል በጉጉት ሲጠበቁ የነበሩ አዳዲስ የአይፎን ሞዴሎችን በዚህ ሳምንት ለገበያ ከማቅረቡ ጋር በተያያዘ፣ ሽያጩን ከፍ አድርጎ ወደ ቀድሞ ደረጃው ሊመለስ እንደሚችል ይጠበቃል ብሏል፡፡
ሁዋዌ ለዚህ ስኬት የበቃው በስማርት ፎን ምርት ኢንዱስትሪው፣ በሰፋፊ የገበያና የማስታወቂያ ስራዎችና በሽያጭ መስመሮች ማስፋፊያ ዘርፎች ላይ በቋሚነት ትልቅ ኢንቨስትመንት በማድረጉ ነው መባሉንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
ኩባንያው ከቅርብ አመታት ወዲህ በአለማችን የስማርት ፎን ገበያ ሽያጭ መሪነቱን ከያዘው የደቡብ ኮርያው ሳምሰንግ ጋር ለመፎካከር ብርቱ ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ ያስታወሰው ዘገባው፤ በኔትወርክ ዝርጋታና በሌሎች ተያያዥ መስኮች ላይ ከነበረው እንቅስቃሴ ወደ ስማርት ፎን ምርት በመዞር ወደ ገበያው ከገባ አጭር ጊዜው ቢሆንም፣ በፍጥነት በማደግ ከታላላቆቹ ሳምሰንግ እና አፕል ጋር ለመፎካከር መብቃቱን ገልጧል፡፡
አፕል ኩባንያ እ.ኤ.አ ከ2010 አንስቶ በአለማችን የስማርት ፎን ሽያጭ ገበያ፣ ከአንደኛ ወይም ከሁለተኛ ደረጃ ዝቅ ብሎ እንደማያውቅም ዘገባው አክሎ አስታውሷል፡፡

  ከዚህ በፊትም ፕሬዚዳንቱን በስልጣን ለማቆየት ህገ መንግስቱ ተሻሽሏል

        በኡጋንዳ የገዢው ፓርቲን የሚወክሉ የፓርላማ አባላት፣ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት የዕድሜ ጣራ 75 አመት እንዲሆን የሚገድበውን የህገ መንግስት አንቀጽ እንዲሰረዝ የሚጠይቀውን የውሳኔ ሃሳብ ባለፈው ማክሰኞ በሙሉ ድምጽ መደገፋቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
የፕሬዚዳንቱን የእድሜ ገደብ ለማስቀረት ያለመው የውሳኔ ሃሳቡ፣ የአገሪቱን ህገ መንግስት በማሻሻል፣ የ72 አመቱን ፕሬዚዳንት ዮሪ ሙሴቬኒ፣ በ2021 በሚካሄደው ቀጣዩ የአገሪቱ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንዲወዳደሩ ለማስቻል የተደረገ ሙከራ ነው ሲሉ ተቃዋሚዎች ትችት መሰንዘራቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡
ፕሬዚዳንት ሙሴቬኒ በቀጣዩ ምርጫ ዕድሜያቸው ከ75 አመት በላይ ስለሚሆን፣ በህገ መንግስቱ መሰረት፣ ለፕሬዚዳንትነት መወዳደር እንደማይችሉ የጠቆመው ዘገባው፤ ፓርቲያቸው ናሽናል ሬዚዝታንስ ሙቭመንት ግን፣ ያለ አግባብ ህግ በማሻሻል በስልጣን እንዲቆዩ ለማድረግ ዘመቻ መጀመሩን አመልክቷል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ከሁለት ወራት በፊት በጉዳዩ ላይ በሰጡት አስተያየት፣ አሁን የዕድሜ ገደብን በተመለከተ የምንወያይበት ጊዜ ላይ አይደለሁም፣ አገር በመምራቱ ላይ ነው ትኩረት የማደርገው ሲሉ መናገራቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡
የዕድሜ ገደቡን የሚያነሳው የውሳኔ ሃሳብ በፓርላማው የሚጸድቅ ከሆነ፣ የፕሬዚዳንት ሙሴቬኒን ስልጣን ለማራዘም ሲባል 20 አመታትን ባስቆጠረው የአገሪቱ ህገ መንግስት ላይ የተደረገ ሁለተኛው ማሻሻያ እንደሚሆን የጠቆመው ዘገባው፤ በ2005 ላይም ሙሴቬኒን በስልጣን ላይ ለማቆየት ሲባል ከሁለት የስልጣን ዘመን በላይ መግዛትን የሚከለክለው የህገ መንግስቱ አንቀጽ መሻሻሉን አስታውሷል፡፡

  “አትቀልዱ ርሃብን የምናሸንፈው ጥንቸል እየበላን ነው” - የግብርና ሚ/ር

        አነጋጋሪው የቬንዙዌላ ፕሬዚዳንት ኒኮላስ ማሩዶ በቅርቡ የምግብ እጥረትን ለመቋቋም ጥንቸል እያረቡ እንዲበሉ ለዜጎቻቸው ያስተላለፉት ምክር ከባህልና እምነት ጋር በተያያዘ ተቃውሞ እንደገጠመው ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
በኢኮኖሚ ቀውስ በተመታችው ቬንዙዌላ፣ በተለይ ህጻናት በከፍተኛ የተመጣጠነ ምግብ እጥረት እየተጎዱ እንደሚገኙ የጠቆመው ዘገባው፤ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ማዱሮም በቅርቡ ባደረጉት ንግግር፣ ዜጎች በመኖሪያ ቤታቸው ጥንቸሎችን እያረቡ ቢመገቡ በቂ የእንስሳት ፕሮቲን ሊያገኙ እንደሚችሉ መምከራቸውንና ጉዳዩ ግን ተቀባይነት አለማግኘቱን አመልክቷል፡፡ ፕሬዚዳንቱ ለአገሪቱ የግብርና ሚኒስቴር ባስተላለፉት መመሪያ፣ በተለያዩ 15 የአገሪቱ አካባቢዎች የጥንቸል እርባታ ፕሮጀክት መጀመሩንና ግልገል ጥንቸሎች ለእርባታ መከፋፈላቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ይሄም ሆኖ ግን ነዋሪዎቹ ከሃይማኖታቸውና ከባህላቸው አንጻር የጥንቸል ስጋ ለመብላት ባለመፍቀዳቸው፣ጥንቸሎቹን አርብተው ለምግብነት ከማዋል ይልቅ ለቤት ማድመቂያነት እየተጠቀሙባቸው እንደሆነ ተረጋግጧል ብሏል፡፡
የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች፣ የፕሬዚዳንቱን የጥንቸል እቅድ “የጅል ቀልድ” በማለት ያጣጣሉት ሲሆን፣ የግብርና ሚኒስትሩ ፍሬዲ በርናል ግን “አትቀልዱ ርሃብን የምናሸንፈው ጥንቸል እየበላን ነው” ማለታቸውን ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

      የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ባለፈው ነሐሴ ወር 2009 ዓ.ም፣ በ23 የግብይት ቀናት፣ የ1.7 ቢሊየን ብር ዋጋ ያለው የሰሊጥ፣ ቦሎቄና ቡና ምርት ማገበያየቱን አስታውቋል፡፡ ምርት ገበያው በአዲስ መልክ በጀመረው የቡና ግብይት ሞዴል እንዲሁም ሰሊጥና ቦሎቄን በሚያገበያይባቸው የኤሌክትሪክ ግብይት ዘዴ፣ በዚህ ወር ብቻ 33,528 ቶን ምርት ማገበያየት መቻሉን ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫው አመልክቷል፡፡
የኢትዮጵያ ምርት ገበያ በዚህ ወር ካገበያያቸው ምርቶች መካከል ቡና 1.40 ቢሊየን ብር ዋጋ ያለው 21,159 ቶን የምርት ግብይት አፈፃፀም በማሳየት፣ በዋጋ 82 በመቶ፣ በመጠን 63 በመቶ የቅድሚያ ደረጃውን ይዟል ብሏል ምርት ገበያው፡፡ ከዚህ ግብይት ውስጥ ለውጪ ገበያ የተዘጋጀ ቡና 15,817 ቶን፣ ለሀገር ውስጥ ፍጆታ 4,152 ቶን፣ ስፔሻሊቲ ቡና 1,190 ቶን ድርሻ አላቸው፡፡ እያንዳንዱ የቡና ዘርፍ በፈረሱላ የተሸጠበት ከፍተኛ ዋጋ ስፔሻሊቲ 2,807፣ የታጠበ ቡና 1550፣ ያልታጠበ ቡና 2,753 ሲሆን ዝቅተኛ ዋጋ ደግሞ ስፔሻሊቲ 950 ብር፣ የታጠበ ቡና 810 ብር፣ ያልታጠበ ቡና 800 ብር መሆኑንም ምርት ገበያው ጠቁሟል፡፡
የነሐሴ ወር የቡና ግብይት ከሐምሌ 2009 አፈጻጸም ጋር ሲነጻጸር የምርት መጠኑ በ52 በመቶ፣ አጠቃላይ የምርት ዋጋው ደግሞ በ66 በመቶ አድጓል ያለው ምርት ገበያው በተለይ ወደ ውጪ የሚላክ ቡና ግብይት መጠን በ66 በመቶ፣ በዋጋ 80 በመቶ ከፍ ብሏል፡፡ ይህም እድገት ከተገኘባቸው ምክንያቶች አንዱ፣ የቡና መገኛን ባለቤትነት የተመረኮዘ የመኪና ላይ ግብይት ሥርዓት፣ በምርት ገበያው መካሄዱ መሆኑን ገልጿል፡
እንዲሁም ከቡና ቀጥሎ ሁለተኛ ደረጃ የያዘው ሰሊጥ ሲሆን 303 ሚሊየን ብር ዋጋ ያለው 11,479 ቆን ግብይት መከናወኑም ተጠቅሷል፡፡ ከአጠቃላይ ገብይቱ በመጠን 34 በመቶ፣ በዋጋ 18 በመቶ ድርሻ አለው፡፡ በኩንታል የነበረው ዋጋም ከፍተኛው 2,906 እንዲሁም ዝቅተኛው 2,200 ብር አውጥቷል፡፡ ከዚህ ውስጥ 205 ሚሊየን ብር ዋጋ ያለው 7,455 ቶን ነጭ የሁመራ ጎንደር ሰሊጥ ግብይት በመፈጸሙ ግንባር ቀደም ቦታ ይዟል ብሏል ምርት ገበያው፡፡
የኢትዮጵያ ምርት ገበያ - የሁሉም ገበያ

 ደራሲ፡-ተሾመ ብርሃኑ ከማል
                                      የታተመው፡-2009
                                      አሳታሚው፡- በግል
                                      የገጹ ብዛት፡- 200     

       የኢትዮጵያና የኤርትራ ጉዳይ  እጅግ ወቅታዊ  አጀንዳ ነው፡፡ ሊተዉ ከማይችሉ  (unavoidable) ርዕሰ ጉዳዮች አንዱና ዋነኛውም ይመስለኛል፡፡ ይህ ጉዳይ የታሪክ፣ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ፣ የማህበራዊ፣ ---ወዘተ ብቻ ሳይሆን የሰው ልጅ ሂደት ማሳያም ጭምር ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ነው በቅርቡ የታተመውን፣ የተሾመ ብርሃኑ ከማል፣ “የሰላም ፍኖት ለኤርትራና ለኢትዮጵያ ህዝቦች አንድነት” የተሰኘ መጽሐፍ፣  ልዳስሰው የተነሳሳሁት፡፡
የኢትዮጵያንና የኤርትራን ሕዝቦች ወቅታዊ ግንኙነት ከግምት በማስገባትም ይመስላል፣ የመንግሥትም ሆነ የሌሎች ፖለቲካ ድርጅቶች ወይም ግለሰቦች ተጽእኖ እንደሌለበት፣ ፕሮፓጋንዳም ሆነ ወገንተኛም አለመሆኑን ስጋት በተመላበት ሁኔታ ይገልጻል፡፡ ይህም ሆኖ፣  የኢትዮጵያና የኤርትራ ሕዝቦች በፖለቲካዊ ድንበር ቢለያዩም በማህበራዊ ኑሮ፣ በቋንቋ፣ በባህል፣ በስነ ልቦና፣ በታሪክ፣… ከጥንት እስከ ዛሬ አንድ መሆናቸውን በማውሳት፣ ወደ ቀዳማዊ አንድነታቸው ተመልሰው ጥንታዊ ታሪካቸውን እንዲያድሱ፣ የሕዳሴ እንቅስቃሴያቸውንም በሕዝቦች የታሪክ እርቅ ላይ እንዲመሠርቱ፣ የታሪክ እርቅን  መሥርተው የሚወስዱት መንገዶች ለሽምግልና የተሻሉ፣ ሰላማዊና ፍትሐዊ መሆናቸውን አውቀው በጋራ እንዲንቀሳቀሱ፣ ሰዎች “እኔ ማን ነኝ?” ብለው በመጠየቅ፣ ማንነታቸውን እራሳቸው እንዲመልሱ … ሐሳብ ለመሰንዘር ይሞክራል እንጂ በኃይል አንድ ይሁኑ ለማለት አይዳዳውም፡፡›› በማለት ከገጽ 7-8 ይገልጽና፣ ‹‹የተወሰኑ የገንጣይ ቡድኖችና ደጋፊዎቻቸው ሴራ ነው›› በሚል እምነት እንዳልተጻፈ፣ ሆኖም አንድ የነበሩ፣ በሥጋ ዝምድና፣ በጋብቻ፣ በማህበራዊና በኢኮኖሚ የተሳሰሩ ሕዝቦች፣ በታሪክ አጋጣሚ ተለያይተዋልና በሰላም ፍኖት እየተጓዙ፣ በመጀመሪያ የኢትዮጵያና የኤርትራ ሕዝቦች ወንድማማችነት ላይ የተመሠረተ ግንኙነት እንዲመሠርቱ፣ ደረጃ በደረጃ፣ ቀስ በቀስ፣ ስልትና ሐቅን በተከተለ መንገድ ከሁሉ አስቀድሞ የተለያዩ ግለሰቦች፣ ቤተሰቦች፣ ማህበረሰቦች፣ ህብረተሰቦች ብሎም ሕዝቦች በመንገድ፣ በስልክ፣ በደብዳቤና በመሳሰሉት እንዲገናኙ፣ ቀስ በቀስም በአንድ ላይ እንዲሆኑ፣ አንድ ሆነውም የተሻለ የጋራ ልማትና ብልጽግና በምሥራቅ አፍሪቃ እንዲያመጡ፣ ቢቻልም በረጅም ጊዜ ሂደት በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊ ኑሮና በፖለቲካ እንዲዋሃዱ፣ ከተዋሃዱም በአፍሪቃ ቀንድ ስመ ገናና ሊሆኑ እንደሚችሉ ገለልተኛ በሆነ የሽምግልና ዓይን ለመጠቆም መሆኑን ያወሳል፡፡   
መጽሐፉ አዳዲስ መረጃዎችን አካትቷል። ከእነዚህም መካከል፡- የኢጣሊያውያን ወደ ኢትዮጵያ መምጣትና ኢጣሊያ በእንግሊዝ ድጋፍ ምጽዋን መያዝ፣ አሰብ በኢጣሊያ ቁጥጥር ስር ስለመሆን፣ የጁሰፔ ሳፔቶ፣ የኢጣሊያ ቅኝ ግዛት ፍለጋና የስለላ ሥራ፣ በሐሰን ቢን አሕመድ፣ በኢብራሂም ቢን አሕመድና በጁሰፔ ሳፔቶ መካከል የተፈረመ ስምምነት፣ በኢጣሊያ መንግሥትና በዓፋር ሱልጣኖች መካከል የተደረጉ ስምምነቶች፣ የኢጣሊያ መንግሥት ንጉሣዊ አዋጅ፣ በጣልያን ንጉሣዊ መንግሥትና በሮባቲኖ ድርጅት መካከል ስለ አሰብ ባለቤትነት ጉዳይ የተደረገ ስምምነት፣ በሱልጣን መሐመድ ሐምፈሬ፣ በንጉሥ ምኒልክና በኢጣሊያ ንጉስ እንደራሴ የተፈረመ ውልና ሌሎችም  ይገኙበታል፡፡
በመጽሐፉ ውስጥ በርካታ አስገራሚ ታሪኮች አሉ፡፡ ለምሳሌ ጁሰፔ ሳፔቶ፣ ከ1811-1895 (እኤአ) የኖረ ኢጣሊያዊ የላዛሪት ሚሽን ተከታይ ሲሆን ይህም የላዛሪት ሚሽን የተባለ ድርጅት፣ ድሆችን በመርዳት ስም ፓሪስ  በ1625 (እኤአ) ውስጥ ሴንት ቪንቸንት ፖል በተባለ የሃይማኖት አባት የተቋቋመ ነበር፡፡ ጁሰፔ ሳፔቶ የላዛሪት ሚሽን ተከታይ የሆነው በ18 ዓመቱ ሲሆን ወደ ምጽዋ ከመምጣቱ በፊትም (በ1837) ወደ ሊባኖስና ግብጽ ሄዶ እንደነበር የሕይወት ታሪኩን የጻፉ ሰዎች ይጠቁማሉ፡፡ ይሁንና ድርጅቱ ለድሆች እርዳታ ለመስጠት የተቋቋመ ይባል እንጅ ያቋቋመው የፖለቲካ ድርጅት እንደነበር ይነገራል፡፡ የታሪኩ ጸሐፊዎች እንደሚገልጹት፤ ወደዚህ ስፍራ የመጣው ከሁለት ፈረንሳውያን ወንድማማቾች ጋር ሲሆን ከእነርሱ ጋር ከ1837 እስከ 1847 ባለው ጊዜ ወደ መሃል ኢትዮጵያ በመግባት በአድዋና በጎንደር ጉብኝት አድርጓል፡፡   
ጁሰፔ ሳፔቶ፤ ፍራነቺሰ ጆቫኒ ከተባለ ሌላ ሚሽነሪ ጋር ኦገስት 23 ቀን 1851፣ በምጽዋ በኩል ወደ ከረን መጣ፡፡ በነዚህ ጸሐፊዎች መረጃ መሠረት፣ የላዛሪት ሚሽን ተልእኮውን ለመፈጸም የመጣው በመጀመሪያው የኢትዮጵያ ጉዞው በጸና ታሞ ወዳገሩ ከተመለሰ በኋላ ነው፡፡ በሁለተኛ ጊዜ ጉብኝቱም እንደ ሚሽነሪ ሳይሆን እንደ ጎብኝ ወደ ምጽዋ በመምጣት፣ ደናኪል (የዓፋር) ጨዋማ ስፍራዎችን፣ ቦጎስንና ሓባብን በ1851 ጎበኘ፡፡ በዚህም ጊዜ ግዕዝ፣ ትግረና ቢለን ቋንቋዎችን በማጥናት መዝገበ ቃላት አዘጋጀ፡፡ ከዚያም ወደ አሰብ መጣ፡፡ በ1858 አጼ ቴዎድሮስ በመንግሥታቸው ላይ ያመጸው አገው ንጉሥን ድል አድርገው፣ በገደሉበት ጊዜ፣ ጁሰፔ ሳፔቶን እስረኛ አድርገው፣ እንደ አስተርጓሚ ይጠቀሙበት ነበር፡፡ ሆኖም አጼ ቴዎድሮስ ከጊዜ በኋላ ነጻ አድርገው ስለለቀቁት ወደ ፓሪስ ተመለሰና በፓሪስ የቤተ መዘክር ሠራተኛ ሆነ፡፡ ስዊዝ ካናል በ1869 ሲከፈትም የኢጣሊያ መንግሥት በቀይ ባህር ዳርቻ እንደ ወደብ የሚጠቀሙበትን ቦታ እንዲያስገኝ አደራ ተሰጠው፡፡ ወደ አሰብ ከመጣ በኋላም የተሰጠውን አደራ ሳያሳውቅ፣ ከዓፋር ሱልጣኖች ጋር ወዳጅ መስሎ በመቅረብ፣ ከአሰብ የተወሰነውን መሬት፣ አፋር ግዛት በሚኖርበት ጊዜ ሊጠቀምበት በውል እንደገዛ፣ ከዚህ ቀደም ባልቀረበ መልኩ በመጽሐፉ ውስጥ ሰፍሮ ይገኛል፡፡
ሲኞር ጁሴፔ ሳፔቶ ኃላፊነቱን ከተወጣ በኋላ ወደ ኢጣሊያ ተመለሰ፡፡ በዚህም ጊዜ ከሚያውቁት ሰዎች ጋር እምብዛም አይገናኝም ነበር፡፡ ሲኞር ጁሴፔ ሳፔቶ ወደ ኢጣሊያ ከተመለሰ በኋላ በአራተኛው ዓለም አቀፍ ኦሪየንታሊስቶች ጉባኤ ላይ፣ በ1878 ተካፋይ ነበር፡፡ በዚህ ጊዜም የተለያዩ ኢትዮጵያን የሚመለከቱ ጥናታዊ ጽሑፎችን አቅርቧል፡፡
ከጁሴፔ ሳፔቶ በፊት የምናገኘው የሃይማኖት ሰው ጉልየሞ ማሳይ፣ በተለምዶ አባ ማስያስ (እ.ኤ.አ 1809-1889) የምንለው ቄስ ሲሆን ይህም ሰው ኢጣሊያ ቦቫ በምትባል ስፍራ የተወለደ ነው። በአገራዊ አባባል፣ አባ ማስያስ የተባለው የካቶሊክ እምነት ተከታይ በኢትዮጵያ በተለይም በደቡብና በደቡብ ምዕራብ ውስጥ ለ25 ዓመታት ኖሯል፡፡
አባ ማስያስ ወደ ኢትዮጵያ የተላከው በጉግሊየሞ ስም ሲሆን ጁሴፔ ከተባለ ሌላ ፈረንሳዊ ጋር በመሆን ወደ ሮም ሄዶ ስለ ኢትዮጵያ ሁኔታ ሪፖርት ካቀረበ በኋላ በ1846 ኦሮሞዎችን ክርስቲያን ለማድረግ በሚል ሰበብ ‹‹የኦሮሞ ቄስ›› ተብሎ እንደገና መጣ፡፡ ድሮውንም አባ ማስያስ እየተባለ የነበረው ኢጣሊያዊ አቡነ ባርቶኔሊ በሚል ስም ወደ ጎጃም ተልኮ እንደነበር እርሱን በሚመለከት የተጻፉ ድርሳናት ያመለክታሉ፡፡ በ1849 ደግሞ ብጹእ ወቅዱስ አቡነ ሞንሲኞር ተባለ፡፡ ይህ ሰው  በ1879  ወደ ሀገሩ የተመለሰ ሲሆን በ1880 በፈረንሳይ በተካሄደው ጉባኤ ላይ በመገኘት ለኦሮሞዎች ተጨማሪ ሚሺነሪዎች እንደሚያስፈልጋቸው አበክሮ የገለጸ ሲሆን በ1884 የካርዲናንነት ሲመት በሮማ ካቶሊክ ቤተክርስቲያን ርእስ ሊቃነ ጳጳሳት በአቡነ ሊዮ 33ኛ (1878-1903). ተሰጠው፡፡ በሀገሩም ውስጥ ሕይወቱ አለፈ፡፡ ይሁንና እርሱ ከሞተ ከ75 ዓመታት በኋላ የኢጣሊያ ፋሽስት የአባ ማስያስ በኢትዮጵያ ውስጥ መኖር ለኢጣሊያ ቅኝ ግዛት መመቻቸት ቅድመ ሁኔታ እንደነበር አስታውቋል፡፡ ነገር ግን አባ ማስያስ ፖለቲካዊ ሚና ይኑረው አይኑረው ያሳየው ፍንጭ አልነበረም።  ዳግማዊ አጼ ምኒልክም የዚህ ሰው ጥሩ ወዳጅ እንደነበሩ የሚታወቅ ሲሆን በአማርኛና በኦሮምኛ ያዘጋጀውን የሰዋስው መጽሐፍ አሳትመውለታል፡፡ አባ ማስያስ ከዚህም በተጨማሪ “በኢትዮጵያ ደጋማ ስፍራዎች በሚሽን የቆየሁባቸው 35 ዓመታት” በሚል ርእስ መጽሐፍ ያዘጋጀ ሲሆን ይህም ስለ ኢትዮጵያውያን ማንነት የሚያወሳ መጽሐፍ በ1936 መታተሙ ይታወቃል፡፡ መጽሐፉ ጠቃሚ ሆኖ በመገኘቱም ወደ እንግሊዝኛ፣ ፈረንሳይኛና ጀርመንኛ ተተርጉሟል፡፡
እነ አባ ጁሴፔ ሳፔቶና እነ አባ ማስያስ በአንድ በኩል ሃይማኖት በሌላ በኩል ደግሞ የፖለቲካ አማካሪ፣ በዋነኛነት ስለ ኢትዮጵያ ሁኔታ ለመንግሥታቸው መረጃ አስተላላፊ ሆነው ሲሰሩ ከቆዩ በኋላ ተልእኳቸውን ሲፈጽሙም ወደ ሀገራቸው እየተጠሩ ሹመት የተቀበሉ ሲሆን  የኢጣሊያ መንግሥት ደግሞ ያገኘውን መረጃ በመጠቀም፣ ቅኝ ግዛት የማስፋፋት ዓላማውን ለማስፈጸም ተጠቅሞበታል፡፡
ስለ ዓድዋ ጦርነት በሚያወሳው ምዕራፍ እንደተጠቀሰው ሁሉ ኢጣሊያ ኢትዮጵያን መውረር የጀመረችው በእነ ጋርባልዲና ማዚኒ ተበታትና የነበረችው ኢጣሊያ፣ በ1861 በተዋሃደች በ17 ዓመታት ውስጥ ነው፡፡ ያኔ ኢጣሊያ ከተዋሃደች በኋላ ብዙዎች ታላቋን ኢጣሊያ የመመስረት ሕልም ነበራቸው፡፡ በወቅቱ የኢጣሊያ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበረው ፍራንሲስኮ ክሪስፒ፤ ኢጣሊያን ትልቅ ማድረግ የሚቻለው በአፍሪካ ውስጥ ቅኝ ግዛት ለማስፋፋት የተቻለ እንደሆነ ነው ብሎ ያምን ነበር። ስለሆነም ቀደም ሲል በተጠቀሰው ውል መሠረት ጁሰፔ ሳፔቶ፣ የአሰብ የተወሰነ ክፍል በ1869 ሲገዛ፣ ዓላማው ለራፌኤሎ ሩባቲኖ ኩባንያ የመርከብ ከሰል መሙያ የነበረ ሲሆን የኢጣሊያ መንግሥት ግን በውሉ ውስጥ የነበሩትን ቀዳዳዎች ተጠቅሞ፣ የቅኝ ገዥነት እግሩን የሚተክልበት ቦታ አደረገው፡፡
ከውህደት ወዲህ የመጀመሪያ ንጉሥ የነበረው ዳግማዊ ቪቶሪዮ ኢማኑኤልም “ኢጣሊያ መከበር ብቻ ሳይሆን መፈራት አለባት” የሚል አቋም ነበረው፡፡ የስዊዝ ካናል በ1869 መከፈት ለኢጣሊያ የንግድ እንቅስቃሴ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማበርከቱ፣ መርከቦቿ የድንጋይ ከሰል ነዳጅ የሚሞሉበትና ዕቃዋን በቅብብሎሽ ወደ ሌሎች አገሮች የምታሻግርበትን ወደብ ትፈልግ ነበር፡፡ በዚህም መሠረት ‹‹ሊጉሬ›› የተባለው የንግድ መርከብ ማህበር (Associazione Marittima Mercantile Ligure) ‹‹ቀይ ባህርን በማቋረጥ እስከ እሩቅ ምሥራቅ አገሮች መጓዝ የሚቻለው በእንፋሎት በሚሄድ መርከብ መሆኑንና እንፋሎት ለመፍጠር የሚያስችለው ድንጋይ ከሰል የሚራገፍበት ወደብ በአፍሪካ ቀንድ ማግኘት እንደሚገባ  ለመንግሥት ሪፖርት ካቀረበ በኋላ፣ ሐሳቡ ተቀባይነትን በማግኘቱ፣ የመንግሥት ባለስልጣናት በጉዳዩ መምከር ጀመሩ፡፡ በአፍሪካ ቀንድ ካሉት ስፍራዎች ያለ ችግር የሚያዙትና ለወደብነት የሚያመቸው የትኛው እንደሆነ ለማወቅ ከዚህ ቀደም ለመልክዓ ምድር ጥናት የላኳቸው ባለሙያዎች ያቀረቡትን መረጃ መመልከት ጀመሩ፡፡ ራፋኤሎ ሩባቲኖ፣ ያኔ ግንባር ቀደሙ የንግድ መርከቦች ኩባንያ ባለቤት ከመንግሥት ጋር መልካም ግንኙነት የነበረው ሲሆን መንግሥትም አዳዲስ የንግድ መስመሮችን በሜዲትራንያንና በቀይ ባህር አካባቢ ባሉ የአፍሪካ አገሮች የባህር ድንበር ላይ እንዲዘረጋ አደራ ጥሎበት ነበር፡፡  ‹‹ውሻ በቀደደው ጅብ ይገባል›› እንዲሉም ሲኞር ጁሰፔ ሳፔቶ ሆን ብሎ በውሉ ውስጥ እርሱ ለመኖሪያነት በገዛው መሬት ላይ ሌሎች የእርሱ ሰዎች መጥተው ቢኖሩ ምንም ዓይነት ተንኮል በአፋሮች ዘንድ እንደማይደርስባቸው ቅዱስ ቁርዓን አስይዞ አስምሏቸው ስለነበር በእርሱ እግር የሩባቲኖ ኩባንያ፣ በሩባቲኖ ኩባንያ እግር፣ የኢጣሊያ ቅኝ ገዥዎች እስከ መጨረሻው እያታለሉና እየሸፈጡ ቦታ ያዙ፡፡ ከፊል አሰብ ለሩባቲኖ ኩባንያ በ1870 ዓ.ም መሸጧን ተከትሎም ዘመናዊ ወደብ ተደርጋ ተሠራች፡፡ ከዘጠኝ ዓመታት በኋላም ኩባንያው ከአሰብ እስከ መሃል ሐበሻ የነበረውን ንግድ ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለማካሄድ የጦር መርከቦች እንደሚያስፈልጉት ገለጸ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ካሮሊም የኢጣሊያ መንግሥት ምክር ቤት የተቀደሰ ሐሳቡን የደገፈው መሆኑን ገልጾ፤ ‹‹ቅኝ ግዛታችንን ለመጠበቅ ሁለት የጦር መርከቦች ልኬልሃለሁ›› የሚል መልእክት አስተላለፈለት፡፡  ክርሲፒ በሁለተኛው ደብዳቤው፣ በአሰብ የንግድ ማዕከል መቋቋሙ የሀገሪቱን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ በማሳደግ በኩል ጠቀሜታ እንደሚኖረው ጠቁሞ፣ በንግዱ ዘርፍ ብቻ ሳይሆን የኢጣሊያን የባህር ኃይል ለማደራጀትም አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ገለጸለት፡፡ ከዚህ ደብዳቤ በግልጽ እንደምንረዳውም፣ ምንም እንኳን ጁሰፔ ሳፔቶ ለመኖሪያነት ገዝቶ ለነዳጅ መሙሊያነት ለራፋኤሎ ሩባቲኒ ቢያስተላልፈውም አሰብ ወደ ኢጣሊያ ቅኝ ግዛትነት የመቀየር ፍላጎት የነበራት መሆኑን ነው፡፡
በዚህም መሰረት፣ በአዋጅ ቁጥር 857፣ በአሰብ የጣልያንን ቅኝ ግዛት በተመለከተ በ5/6/1882 ዓ.ም በወጣ አዋጅ ነጋሪት ጋዜጣ ቁጥር (160/10/7/1882 ዓ.ም) ‹‹ቀዳማዊ ኡምቤርቶ የጣልያን ንጉሥ፣ የሕዝብ እና የዘውድ ምክር ቤቶች የተስማሙበትን በማጽደቅ ከዚህ ቀጥሎ የቀረበውን አወጀች፡፡ በዚህም አዋጅ፣ ከቀይ ባሕር በስተደቡብ ምዕራብ ጠረፍ የምትገኘዋ የአሰብ ክልል፣ የጣልያን ቅኝ ግዛት ሆኖ በጣልያን መንግሥት ሥር እንድትተዳደር ተደርጓል፡፡ ክልሉም ከራስ ደርሚክ እስከ ራእስ ሎማ ድረስ ያለው ስፋቱ ስድስት ማይልስ፣ ከራስ ሎማ እስከ ራስ ደውራን ድረስ ያለው ስፋቱ ሁለት ማይልስ የሆነ፣ ከሼክ ደውራን አስኮ ራእስ ሣንቶራ ድረስ ያለው ስፋቱ አራት ማይልስ የሆነ፣ ከራስ ሎማ ፊት ለፊት የሚገኘው የሠንዓቡር ደሴት፣ ከጠረፍ ፊት ለፊት የሚገኙ ደሴቶች- ከራስ ሉማ እና ከራእስ ሣንቱር ፊት ለፊት ያሉትን ያጠቃልላል፡፡ በጣልያን መንግሥትና በሩባቲኖ ድርጅት መካከል በማርች 10/1882 ተደርጎ የነበረው ስምምነት ስለጸደቀ፣ በስምምነቱም መሠረት፣ የድርጅቱ ንብረት ወደ ጣልያን መንግሥት ተሸጋግሯል፡፡›› ንጉሥ ኡምፔርቶ፣ ጁላይ 5 ቀን 1882 ሮማ፡፡
ከዚህም አዋጅ በኋላ በምድረ ኤርትራ ስለተሾሙት የኢጣሊያ ባለስልጣኖች ስም ዝርዝር በመጽሐፉ ውስጥ እናገኛለን፡፡ ‹‹የፈሩት ይደርሳል የጠሉት ይወርሳል›› እንዲሉ፣ የኢጣሊያ መንግሥት በ1882 ላይ አሰብ ቅኝ ግዛቱ መሆኗን አስታወቀ። ከሁለት ዓመታት በኋላም የውጭ ጉዳይ ሚንስትሯ ሲኞር ማቺኒ፣ የሸዋው ንጉሥ ምኒልክ፣ አሰብ ወደብን ከአውሮፓ ገበያ ጋር በቀጥታ የሚያገናኛቸው ማዕከል አድርገው ያለ አንዳች ችግር እንዲጠቀሙበት ጋበዘ፡፡ በእርግጥም አሰብ ለማደግ ከኢትዮጵያ ወደ ውጭ የሚሄድና ከውጭ ወደ ኢትዮጵያ የሚገባ ንግድ ያስፈልጋት ነበር፡፡
በመጽሐፉ ውስጥ መሠረታዊው ዓላማው የሽምግልና ጉዳይ በመሆኑ፣ ከሁሉ አስቀድሞ ኤርትራውያን ስለ ራሳቸው ምን እንደሚሉ ማወቅ እንደሚገባ ይገልጻል፡፡ በዚህም መሠረት ኤርትራውያን እንደሚሉት፤ ‹‹ኤርትራ ከሰሜን ሱማሊያ፣ ከጅቡቲና ከቀይ ባሕር ድንበር የሆነው የሱዳን ግዛት ጋር በመደመር የፑንት ግዛት ተብላ ጥንት በጥንት ግብጻውያን ዘንድ ትታወቅ ነበር። ትርጉሙም ምድረ እግዚአብሔር ማለት ነው። ስለዚችም አገር በታሪክ ምዕራፍ የሚጠራው ከክርስቶስ ልደት በፊት ከ25ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ ነው፡፡ ጥንታዊ የፑንት ግዛት ነዋሪዎች፣ ከጥንታዊዋ የፈርኦን ስርወ መንግሥት ጋር ግንኙነት የነበራት ሲሆን በተለይም በንጉሥ ሳሁርና በንግሥት ሐትኮፐስት ዘመን ግንኙነቷ ጠንካራ ነበር፡፡ ያኔም በተለይም ከስምንተኛውና ሰባተኛው ክፍለ ዘመን (ቅድመ ልደት) ደዓማት የሚባል መንግሥት በኤርትራና በኢትዮጵያ ነበር። ዋና ከተማውም ይሃ ተብሎ በሚጠራው ስፍራ ሲሆን በዚህም ጊዜ የነበረው መንግሥት በመሥኖ  እርሻ ያለማ፣ የብረታ ብረት ቁሳቁሶችንና የጦር መሣሪያዎችን ይሠራ ነበር፡፡ የደዓማት ሥርወ መንግሥት ከ5ኛው ክፍለ ዘመን (ቅድመ ልደት) ከወደቀ በኋላ የአክሱም ስርወ መንግሥት በ1ኛው ክፍለ ዘመን ተመሥርቶ እስኪያስተባብራቸው ድረስ አነስተኛ ነገሥታት በተበታተነ መልክ አካባቢያቸውን (የጥንቷን ኤርትራንና ኢትዮጵያን) ያስተዳድሩ ነበር፡፡ በኢጣሊያ ጊዜም ሆነ ከዚያ በፊትና በኋላ አፋሮች በኤርትራ መሬት ምንም አያገባቸውም፡፡ ባሕረ ነጋሽ፣ ትግራይ ትግረኝ የሚባለው ማዕረግና ብሔረሰብ ያልነበረ ዝም ብለው ሰዎች የፈጠሩት ነው፡፡ ስለዚህ ኤርትራን ባህረ ነጋሾች አላስተዳደሯትም፡፡››  
---በ1920ዎቹ መጀመሪያ ላይ ላይ የኢጣሊያውንና የሌሎችን ነጮች የበላይነት፣ የኤርትራውያንና የሌሎች ጥቁሮችን የበታችነት በግልጽ የሚደነግግ አዋጅ አወጀ፡፡ ይህም በአንድ አገር ውስጥ ሁለት ሕግ እንዲኖር አስቻለ፡፡ በዚህ አዋጅ መሠረትም፣ ነጮችና ጥቁሮች በአንድ ሆቴል ውስጥ ተቀምጠው መመገብ አቆሙ፡፡ ጥቁሮችና ነጮች የተለየ የትራንስፖርት አገልግሎት መጠቀም ጀመሩ፡፡ ነጮች እንዲቀመጡባቸው በተከለሉት መንደሮች ጥቁር ኤርትራውያኖቹ እንዳይኖሩ ተከለከሉ፡፡ ጥቁሮቹ ኤርትራውያንና በኤርትራ ውስጥ የሚኖሩ ሌሎች ጥቁሮች ከነጮች ጋር በሕግ ፊት እኩል የመሆናቸው ነገር አበቃ፡፡ ነጮችና ጥቁሮች ለየብቻ መዳኘት ጀመሩ፡፡ ጥቁሮች በነጮች በደል ቢደርስባቸው እንደ በደል መታየት አቆመ፡፡ በወቅቱ የነበሩ ብዙዎቹ ኤርትራውያን ትምህርቸው ከአንደኛ ደረጃ ከፍ እንዳይል ተደረገ፡፡ ይህም ትምህርት በአመዛኙ ከኢጣሊያውያን ገዥዎቻቸው ጋር በቋንቋ ለመግባባትና ለመታዘዝ እንዲችሉ እንጅ ዕውቀት እንዲያገኙ የሚያስችል አልነበረም፡፡ ይህም ኤርትራውያንና በኤርትራ የሚኖሩ ጥቁሮች የበለጠ በጭቆና እንዲገዙ አደረጋቸው፡፡ የፋሽስታዊ አገዛዙ ስልትም በጦር ቃል ኪዳን አገሮች ጫና በደረሰበት ቁጥር እየጨመረ ሄደ እንጅ አልቀነሰም፡፡
ይህም ሆኖ ደግሞ በኤርትራውያኑ መካከል የነበረው የመደብ፣ የዘር፣ የጎሳ፣ የቋንቋ፣ የጾታ፣ የዕድሜ፣ የእምነት ልዩነት እንዲሰፋና እርስ በእርሳቸው እንዲናናቁ የሚያስችል ስልት ቀየሰ። በተለይም ከአገዛዙ ጋር አንስማማም ብለው ወደ ኢትዮጵያ በመግባት የከዱት መሬት የደመኛ መሬት እየተባለ ይወሰድ ጀመር፡፡ ከበስተጀርባቸው ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን እንዳሉ የሚያውቁት የነቁ ኤርትራውያን፣ ኢጣሊያን እየከዱ ወደ ኢትዮጵያ መምጣትና መውጋት ጀመሩ፡፡ ኢትዮጵያን ጠቅልላ ካልያዘች እረፍት እንደማይኖራት የተገነዘበችው ኢጣሊያም በ1928 ላይ ሠራዊቷን ወደ ኢትዮጵያ አዘመተች፡፡  በ1933 በእንግሊዝ እስክትሸነፍ ድረስም ቆየች፡፡ ከዚያም በመጽሐፉ ውስጥ በሚተነተነው ሰፊ ምክንያት ከኢትዮጵያ ጋር ተዋሃደች፡፡
በመሠረቱ፣ በኤርትራውያንና በኢትዮጵያውያኑ ትግሬዎች መካከል የብሔር፣ የቋንቋ፣ የሃይማኖት አንድነት ቢኖርም ኢጣሊያ በገነባችው የጥላቻና የንቀት አመለካከት ሳቢያ ትግሬዎችንና አማሮችን አጥብቀው ይንቁ፣ ያንቋሽሹ ነበር፡፡ በተለይም፣ በኤርትራውያንና በሰሜን ትግራይ ሕዝብ መካከል ጥላቻ እንዲዳብር ያደረጉባቸው መንገዶች በርካታ ናቸው፡፡ ቀንደኛ ባንዶቻቸው ከትግሬዎች በእጅጉ እንዲጠነቀቁ ማድረግ አንዱ ነበር፡፡ ይህም የሆነበት መሠረታዊ ምክንያት ኤርትራውያን ሰፍኖ በነበረው ዘረኛ አመራር እየተበሳጩ ከሰሜን ትግራይ ወገኖቻቸው ጋር እየተገናኙ አደጋ ያደርሱባቸው ስለነበር ነው፡፡ የኢጣሊያን ሀብትና ንብረት ጨለማ ለብሰውና ጫካ ጥሰው ወደ ወገኖቻቸው ያሻግሩ የነበረ ሲሆን ከጌቶቻቸው ጋር ተጣልተው ሲመጡ እጃቸውን ዘርግተው ይቀበሏቸው ነበር። ከዚህም በተጨማሪ  የሰሜን ትግራይ ሰዎች አመችም ሲሆን ድንበሩን ተሻግረው የጠላትን ሀብት ከመዝረፋቸውም በላይ የኢጣሊያ ቅኝ ገዥዎችን ሲቃወሙ ያለ አንዳች ማወላወል የሚመጡት ወደ ትግራይ ዘመዶቻቸው ዘንድ ስለነበር ከትግሬዎች እንዲጠነቀቁ ቢመክሩ የሚደንቅም፣ የሚገርምም ሊሆን አይችልም፡፡ ብዙዎቹ ኤርትራውያን፣ በተለይም ከሰሜን ትግራይ ሕዝብ ጋር የሥጋ ዝምድና፣ የጋብቻ ዝምድናና የእምነት ዝምድና ስላላቸው ባይቀበሉትም አንዳንዶቹ ግን እራሳቸውን ማራቃቸውና የትግራይ ሕዝብን ማጥላላታቸው አልቀረም፡፡ ኢጣልያውያን ቅኝ ገዥዎቹ ወጥተው እንግሊዝ በሞግዚትነት ታስተዳድር በነበረችበት ጊዜም የዘረኛነት አመለካከቱ እንዲቀጥል ተደርጎ የነበረ ሲሆን ለዚህም ጥሩ ማስረጃ የሚሆነው  የከተማው አስተዳደር፣ ሕግ አስከባሪዎች፣ ዳኞችና ባለኢንዱስትሪዎቹ ኢጣሊያውያን ሆነው እንዲቀጥሉ ማድረጋቸው ነው፡፡
መጽሐፉ ከዚህም ሌላ፣ በኤርትራ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች ስለሆኑት  ወልደአብ ወልደማርያም፣ ራቢጣ አል-ኢስላሚያ፣ ዓብዱልቃድር ከቢረ፣ ኢብራሂም ሱልጣን ዓሊ፣ ኢድሪስ ሙሐመድ አደም፣ ሙሐመድ ሰዒድ ናዋድ፣ ሐሚድ ኢድሪስ ዓዋተ፣ ከአሚዶ ጉሌት ምን ያህል ያውቃሉ? አቶ ታምራት ላይኔን ጥርስ ውስጥ ያስገባቸው ጋዜጣዊ መግለጫ የቱ ነው? የኢትዮጵያ መንግሥትና የኤርትራ መንግሥት ወዳጅነት ለምን ምች እንደመታው ሰብል በአንድ ጊዜ ወየበ? የሚሉትን መሠረታዊ ጥያቄዎች በማንሳት ይተነትናል፡፡    
መጽሐፉ ከዚህ ቀደም ተነስቶ በማያውቅ ሁኔታ የኢሕአዴግ ትግልና የኤርትራ ነፃነት ትግልን፣ የኢህአዴግ አነሳስና እድገትን፣ በትግሬዎች ላይ ላለፉት መቶ ዓመታት የሚነዛው ቅኝ ገዥ ወለድ አስከፊ የንቀትና የጥላቻ አመለካከትን፣ የትግራይ ትግርኝ አጭር ታሪክን --- ከመተንተኑም በላይ ህወሓት፣ ኤርትራ ከኢትዮጵያ ለምን እንድትነጠል ፈለገ? ምንስ ጥቅም አስገኘ? (በመላምት ላይ የተመሠረተ ሐሳብ)፣ የሕዝባዊ ወያኔ የፖለቲካ መሪዎች ለምን የውሕደቱን ፍላጎት ትኩረት የሚነፍጉበት ጊዜ ተከሰተ? ምንስ ጥቅም አስገኘ? ---- የሚሉትን ጥያቄዎች  ለመመለስ ይሞክራል፡፡   
ከዚህ ቀደም ታትመው ለንባብ ከበቁ መጻሕፍት የማናገኘው ሌላው ክፍል፣ የኢህአዴግ አሸናፊነትና የሽግግር መንግሥት መቋቋምን፣ በተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ የያዙ የፖለቲካ ድርጅቶችን፣ በተወካዮች ምክር ቤት ከተከናወኑት ሥራዎች በከፊል፣ ለኤርትራ ሬፈረንደም በኤርትራ ጊዜያዊ መንግሥት በኩል የተደረገ ዝግጅትን፣ በሬፈረንደሙ ዋዜማ የኤርትራ ሬፈረንደም ውጤት አቀባበል አጭር ታሪክን፣ የኤርትራን ሬፈረንደም እንዲታዘብ የተላከው የኢትዮጵያ ሽግግር መንግሥት ልዑካን፤ በአስመራ ከተማና አካባቢው፣ በምጽዋና አካባቢው፣ በከረን፤ አቆርዳትና አካባቢው፣ በአካለ ጉዛይና ሠራዩ አውራጃዎች ያነጋገራቸው የተለያዩ የኀብረተሰብ ክፍሎች አስተያየት በዝርዝር ያቀርባል፡፡ የኤርትራን ሬፈረንደም እንዲታዘብ የተላከው የኢትዮጵያ ሽግግር መንግሥት የልዑካን ቡድን አባላት እነማን እንደነበሩም ያመለክታል፡፡
መጽሐፉ ኢትዮጵያና ኤርትራ በሰበበ ባድመ፣ በግጭት ዋዜማ የነበራቸውን ግንኙነትን በሚመለከትም የኤርትራና የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ፣ የማህበራዊና የፖለቲካ ውህደት የምሥራች መግለጫ፣ ድንገተኛው የአቶ ታምራት ላይኔ ጋዜጣዊ መግለጫና ለእስር መዳረግ፣ የብር ኖት መቀየር፣ ኤርትራ የኢትዮጵያን ብር በናቅፋ የሚተካ አዋጅ ማውጣት፣ ፕሬዚደንት ኢሳያስ አፈወርቂ፤ የኢትዮጵያና የኤርትራ ግንኙነት ድንበር የለሽ እየሆነ መምጣቱን መግለጣቸውና በኋላም ‹‹ለኢኮኖሚ ችግራችን ኢትዮጵያን አንወቅስም›› ማለታቸው፣ የባድመ ጦርነት የድንበር ጥያቄ ወይስ ኤርትራን በሚገባ የማስገንጠል ዘዴ? የሚሉትን በዝርዝር ይዳስሳል፡፡
በመጨረሻም መጽሐፉ፣ የሌሎች አገሮች የሰላም ፍኖትን እንደ አብነት በመውሰድ (የቬትናም፣ የጀርመንና የየመን ውህደት ታሪክ) የኢትዮጵያንና የኤርትራ ሕዝብን አንድነት ለማምጣት የሚያስችለውን ጥቅል-የማንነት ጥያቄን ይፈትሻል። የታሪክ እርቅን ለማምጣት ምን መደረግ አለበት? ጥላቻ ምንድን ነው? ጦርነት የሚያስከትለው ጥላቻ፣ መታረም ያለበት እጅግ አደገኛ አዝማሚያ፣ የሰዎች ጥላቻ የመጨረሻ ደረጃ፣---- የመሳሰሉትን መሠረታዊ ጉዳዮች ይተነትናል፡፡ መልካም ንባብ፡፡