Administrator
“ሁሉም ሰው የራሱን ሃላፊነት እንዲወስድ እጠይቃለሁ”
አትሌት ኃይሌ ገ/ስላሴ
ባለፈው ዓመት የያዝናቸውን የስራ እቅዶች ከሞላ ጐደል ማከናወን ችለናል፡፡ ለአዲሱ አመት የተላለፉም አሉ፡፡
በአጠቃላይ 2006 መጥፎ አመት አልነበረም፤ ጥሩ ነበር ብዬ አስባለሁ፡፡
በአዲሱ ዓመት ሁሉም ሰው ሃላፊነት እንዲወስድ እጠይቃለሁ፡፡ ሃላፊነትን መውሰድና መወጣት ቀላል ነገር
ይመስላል እንጂ ከባድ ነው፡፡ ለምሣሌ ስለ መኪና አደጋ ችግር ሲነሳ ጥፋቱ ሁሌም በአንድ ወገን (ሹፌሩ) ላይ
ብቻ ነው የሚደመደመው፡፡ ሃላፊነቱ ለአንድ ወገን ብቻ እየተሰጠ ስለሆነ በዚህ ረገድ ውጤታማ መሆን
አልተቻለም፡፡ ነገር ግን መንገደኛው (እግረኛው)፣ የእንስሳት መንገድ አጠቃቀም፣ የመኪናው ቴክኒካዊ ብቃት
የመሳሰሉትን ሁሉ የሚመለከት ነው፡፡ መንግስትም ሃላፊነቱን እኔ ብቻ እወስዳለሁ ሣይል ወደ ህብረተሰቡም
ማውረድ አለበት፡፡ ያ ካልሆነ የምንመኘው ነገር ውጤታማ ላይሆን ይችላል፡፡
2006 ዓ.ም እውነቱን ለመናገር ለስፖርቱ ጥሩ አልነበረም፤ በአትሌቲክስም ሆነ በእግር ኳሱ፡፡ በዚህ ዘርፍም
ለውጥ እንዲመጣ ሁሉም የየራሱን ሃላፊነት ወስዶ ግዴታውን በሚገባ መወጣት አለበት፡፡ አዲሱ ዓመት
የእድገትና የብልፅግና እንዲሆን መልካም ምኞቴ ነው፡፡
የመጀመሪያዋ በጐ ፈቃደኛ የኢቦላን የሙከራ ክትባት ወሰደች
አሜሪካ 300 ወታደሮች ወደ ላይቤሪያ ልትልክ ነው
እንግሊዛዊቷ የኮሙኒኬሽን ባለሙያ ሩት አትኪንስ ሰሞኑን በኦክስፎርድ ለ60 በጎ ፍቃደኞች ሊሰጥ የታቀደውን
የኢቦላ ቫይረስ የሙከራ ክትባት በመውሰድ የመጀመሪያዋ በጎ ፈቃደኛ እንደሆነች መሆኗን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የሙከራ ክትባቱን የሚወስዱ በጎ ፈቃደኞች እንደሚፈለጉ በቢቢሲ ሬዲዮ መስማቷን የገለፀችው አትኪንስ፣
በምዕራብ አፍሪካ ሁኔታው በጣም አሳዛኝ ስለሆነና የዚህ ክትባት ሂደት አካል መሆን ትልቅ ውጤት ለማምጣት
በሚደረገው ጥረት ማበርከት የምችለው ትንሹ ነገር እንደሆነ በማሰብ፣ ክትባቱን በበጎፈቃደኝነት ለመውሰድ
ወስኛለሁ” ብላለች፡፡
ክትባቱ ከኢቦላ ቫይረስ ትንሽ የዘረመል ንጥረ ነገር ብቻ የያዘ በመሆኑ ተከታቢው በበሽታው እንደማይያዝ
የተገለፀ ሲሆን በኦክስፎርድ የጄነር ኢኒስቲቲዩት ዳይሬክተርና የሙከራ ክትባቱ መሪ የሆኑት ፕሮፌሰር አድርያን
ሂልም፤ “ይሄ ክትባት ማንንም ኢቦላ ያስይዛል የሚል ቅንጣት ስጋት የለም” ብለዋል፡፡
ክትባቱን ለመወጋት ስታስብ የደህንነቷ ጉዳይ እንዳላስጨነቃት የተናገረችው ሚስ አትኪንስ፤ የ15 ዓመት ታዳጊ
ልጇ የኢቦላ ቫይረስ ተሰጥቷት የምትሞት መስሎት እንደነበርና እንዳረጋጋችውም ገልፃለች፡፡
ብዙ ጊዜ አዲስ ክትባት ጥቅም ላይ እንዲውል ፈቃድ ከማግኘቱ በፊት ለዓመታት በሰዎች ላይ ሙከራ ሲደረግ
ይቆይ ነበር ያለው ቢቢሲ፤ በምዕራብ አፍሪካ የተከሰተው የኢቦላ ወረርሽኝ አጣዳፊነት ግን ይሄ የሙከራ ክትባት
በአስደናቂ ፍጥነት ጥቅም ላይ እንዲውል ጥረቱ እንዲጠናከር አድርጓል ብሏል፡፡
በሰዎች ላይ የሚደረገው ሙከራ ውጤታማ ሆኖ ከተገኘ፣ ክትባቱ በፈረንጆች ዓመት መጨረሻ ላይ በቫይረሱ
በተጠቁ አካባቢዎች የሚገኙ የጤና ሰራተኞችን ከበሽታው ለመከላከል ጥቅም ላይ እንደሚውል ታውቋል፡፡
ያን ጊዜ ግን ለ10ሺ ሰዎች ያህል የሚሆን ክትባት እንደሚያስፈልግ የተገለፀ ሲሆን በምዕራብ አፍሪካ ክፉኛ
የተጠቁ አካባቢዎች ላይ የሚሰሩ የጤና ባለሙያዎችን ከቫይረሱ ለመከላከል ጥቅም ላይ ይውላል ተብሏል፡፡
ክትባቱ እየተሰራ የሚገኘው ግላክሶስሚዝክላይን በተባለ ኩባንያና በአሜሪካ ብሔራዊ የጤና ተቋም ሲሆን፣
የእንግሊዝ ዓለምአቀፍ የልማት ተራድኦ ድርጅትን ጨምሮ የተለያዩ የምርምር ተቋማት ለሙከራ ክትባቱ የገንዘብ
ድጋፍ እንዳደረጉ ታውቋል፡፡
በሌላ በኩል የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ የኢቦላ ቫይረስን ለመከላከል እገዛ የሚያደርጉ 3ሺ ወታደሮችን
ወደ ላይቤሪያ የመላክ ዕቅድ እንዳላቸው ባለፈው ማክሰኞ አስታወቁ፡፡ ኦባማ ይሄን ያስታወቁት የላይቤሪያዋ
ፕሬዚዳንት አለን ጆንሰን ሰርሊፍ በሽታውን ለመከላከል እገዛ ያደርጉላቸው ዘንድ ለኦባማ በቀጥታ ያቀረቡትን
ጥያቄ ተከትሎ እንደሆነ ታውቋል፡፡
የአሜሪካ ወታደራዊ ሃይል የህክምና ማዕከሎችን ግንባታ በመቆጣጠርና የጤና ሰራተኞችን በማሰልጠን
ለላይቤሪያ መንግስት እገዛ እንደሚያደርግ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
በምዕራብ አፍሪካ ለተከሰተው የኢቦላ ወረርሽኝ የዓለምአቀፉ ማህበረሰብ ፈጣን ያልሆነ ምላሽ ትችት ሲሰነዘርበት
፣ቆየቱ ይታወቃል፡፡
በበሽታው ክፉኛ የተጠቁት የምዕራብ አፍሪካ አገራት ሴራሊዮን፣ ላይቤሪያና ጊኒ ሲሆኑ ወረርሽኙ ከ2400 በላይ
ሰዎችን ለህልፈት እንደዳረገ ተጠቁሟል፡፡ ከእዚህ የሞት አደጋ ውስጥ ግማሹ የተከሰተው በላይቤሪያ ነው፡፡
የዓለም ጤና ድርጅት፤ አገሪቱ በሺዎች የሚቆጠሩ ተጨማሪ ሰዎችን በቫይረሱ ልታጣ እንደምትችል በቅርቡ
አስጠንቅቋል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ኃላፊዎች፣ በጄኔቫ በሚያካሂዱት ስብሰባ ለወረርሽኙ
በተሰጠው ዓለም አቀፍ ምላሽ ላይ እንደሚወያዩ ቢቢሲ ጠቁሟል፡፡
የጋና ፕሬዚዳንት ጆን ድራማኒ ማሃማ ባለፈው ሰኞ ወረርሽኙን አስመልክቶ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤
“በምዕራብ አፍሪካ ለተከሰተው የኢቦላ ወረርሽኝ ከፍተኛና ፈጣን የውጭ እርዳታ ያስፈልጋል” ብለዋል፡፡
ከኢቦላ ያገገሙ ታማሚዎች ደም በድብቅ እየተሸጠ ነው
የኢቦላ ቫይረስ በተስፋፋባቸው የምዕራብ አፍሪካ አገራት በበሽታው ተይዘው የነበሩና ከህመማቸው ያገገሙ
ሰዎች ደም፣ ታማሚዎችን ለማከም በሚል በድብቅ እየተሸጠ መሆኑን ሲኤንኤን ከትናንት በስቲያ ዘገበ፡፡
የአለም የጤና ድርጅት ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በበሽታው ተይዘው ያገገሙ ሰዎች ደም በውስጡ የኢቦላ
ቫይረስን የሚያጠፋ ንጥረ ነገር አለው በሚል እየተናፈሰ ባለው መረጃ የተነሳ፣ በአገራቱ የሚገኙ የኢቦላ
ታማሚዎች ደሙን በድብቅ ከሚሸጥበት ስውር ገበያ እየገዙ ይገኛሉ፡፡
የአለም የጤና ድርጅትን በሽታው በተስፋፋባቸው የምዕራብ አፍሪካ አገራት እየተከናወነ ያለውን ስውር የደም
ሽያጭ ለማስቆም ከአገራቱ መንግስታት ጋር በመተባበር እየሰራ እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፤ ታማሚዎች
በአገራቱ ሆስፒታሎች በሚሰጠው ህክምና ተስፋ በመቁረጥ ፊታቸውን ወደዚህ ህገወጥ ገበያ ማዞራቸውን
ገልጿል፡፡ ዘ ቴሌግራፍ በበኩሉ፤ ምንም እንኳን ከበሽታው ያገገሙ ሰዎች ደም ታማሚዎችን ቶሎ እንዲድኑ
በማድረግ ረገድ አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ ቢረጋገጥም፣ ደሙ ኤችአይቪ ኤድስን በመሳሰሉ ቫይረሶች የተበከለ
መሆን አለመሆኑ ሳይረጋገጥ በድብቅ የሚሸጥ መሆኑ ሌላ ቀውስ እንዳያስከትል ስጋት መፍጠሩን ዘግቧል፡፡
የአለም የጤና ድርጅት ቃል አቀባይ ማርጋሬት ሃሪስን ጠቅሶ፣ ድርጅቱ ከኢቦላ በሽታ ያገገሙ ሰዎችን ደም
በአግባቡ መርምሮ በመሰብሰብና በማጠራቀም ለተመሳሳይ ህክምና ለማዋል የሚያስችል ደህንነቱ የተጠበቀ
አሰራር እየቀየሰ እንደሚገኝ የዘገበው ዋሽንግተን ፖስት በበኩሉ፣ ድርጅቱ መሰል የደም ህክምናን እንደሚደግፍ
ቃል አቀባይዋ መናገራቸውን አስታውቋል፡፡
“ስውር ስፌት ቁ.2” ተመረቀ
በጋዜጠኛ፣ ገጣሚና ተርጓሚ ነቢይ መኰንን የተጻፈው “ስውር ስፌት ቁ.2” የግጥም መድብል ትናንት ምሽት
በዋቢ ሸበሌ ሆቴል አዳራሽ ተመረቀ፡፡የኪነጥበብ ቤተሰቦችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት
በተከናወነው የምረቃ ስነ ስርዓት ላይ፣ ገጣሚውን ጨምሮ አንጋፋና ወጣት ገጣሚያን ስራዎቻቸውን ለታዳሚው
አቅርበዋል፡፡
ገጣሚ ነቢይ በመኰንን ከዚህ በፊት “ጥቁር፣ ነጭ ግራጫ ግጥሞች” እና “ስውር ስፌት ቁ.1” የግጥም መፃህፍት
ለአንባቢ ያበረከተ ሲሆን፣ በታዋቂዋ አሜሪካዊት ደራሲ ማርጋሬት ሚሼል የተጻፈውን “Gone With The
Wind” የተሰኘ ተወዳጅ የረጅም ልቦለድ መጽሃፍ፣ “ነገም ሌላ ቀን ነው” በሚል ርዕስ ወደ አማርኛ ተርጉሞ
በማቅረብ ይታወቃል፡፡
“ስውር ስፌት ቁ.2” በመጽሃፍት መደብሮችና በአዟሪዎች እየተሸጠ ይገኛል፡፡
“የጭቃ ጅራፎች” ነገ ይመረቃል
“መንገድ ተዘረጋ
መንገድ ተቀየሰ
በተራማጅ እጦት
መልሶ ፈረሰ!...”
በገጣሚ አክሊሉ ገብረ መድህን የተጻፈው “የጭቃ ጅራፎች” የተሰኘ የግጥም መጽሃፍ፣ ነገ ከምሽቱ 11፡30 ሰዓት
በዋቢ ሸበሌ ሆቴል አዳራሽ ይመረቃል፡፡
በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጠነጥኑ 50 የገጣሚው የግጥም ስራዎች የተካተቱበት መጽሃፉ 92 ገጾች
ያሉት ሲሆን በተለያዩ መጽሃፍት መደብሮችና አዟሪዎች ዘንድ በ20 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡
የጥበብ አፍቃሪዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በሚገኙበት የመጽሃፉ የምረቃ ስነ ስርዓት ላይ፣ አንጋፋና
ወጣት ገጣሚያን ስራዎቻቸውን ያቀርባሉ፡፡
የ“ነጻ አርት ቪሌጅ” የስዕል ትርዒት ዛሬ ይከፈታል
“ነጻ አርት ቪሌጅ” በማካሄድ ላይ የሚገኘው ‘ነጻ ሃሳብ’ የተሰኘ የሥነ ጥበብ ፌስቲቫል አካል የሆነው የስዕል ትርዒት ዛሬ ከቀኑ 9 ሰዓት በ“ነጻ አርት ቪሌጅ” ይከፈታል፡፡ነጻ አርት ቪሌጅ ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ እንዳለው፣ ከዛሬ ጀምሮ ለተመልካች ክፍት በሚሆነው በዚህ የስዕል ትርኢት ላይ በ30 ሰዓሊያን የተሰሩ የሥነ ጥበብ ስራዎች ለእይታ ይቀርባሉ፡፡
ከግቢ ‘በሮች’ ወደ መንደር ‘በሮች’…
እንዴት ሰነበታችሁሳ!
እኔ የምለው…ግድግዳው ላይ ያለው ቀን መቁጠሪያ ተለወጠ? እኛ አገር ዘመን መለወጥ ማለት ግድግዳ ላይ ያለውን ቀን መቁጠሪያ መለወጥ ከሆነ እየሰነበተ ነዋ! የምር እኮ…ዘንድሮ “ሲጋራ አቆማለሁ…” “ቂማ አቆማለሁ…” “መጨለጥ አቆማለሁ…” የሚል አንድም ወዳጅ አልገጠመኝም፡፡ ወዳጆቼ ‘ሲፑ’ና ‘ቂማው’… ይሄን ያህል ተስማምተዋችኋል እንዴ! “ነገር እየሰማሁና እያየሁ ከምቃጠል ሳላይና ሳልሰማ እየቃምኩና እየጠጣሁ ብቃጠል ይሻለኛል!” ያልከን ወዳጃችን ጭራሽ እየወፈርክ ሄድክሳ! እውነትም “አለማየትና አለመስማትን የመሰለ ነገር የለም…” ምናምን የሚል የጥናት ውጤት የሆነ ቦታ ሊኖር ይችላል፡፡ ሀሳብ አለን…እንዲህ መፋጠጥ በተለመደበት ዘመን በየምግብ ቤቱ “ሌላው ተመጋቢ የሚመገበውን እየተንጠራሩ ማየት የተከለከለ ነው…” ምናምን የሚል ማስታወቂያ ይለጠፍልንማ!! ስሙኝማ…ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ሰዎቹ ምን የሚሉ ይመስለኛል መሰላችሁ… “አየሻት ስቴክ እኮ ነው የምትበላው!” “ታዲያ ስቴክ ብትበላ ምን አለበት?” “ምን አለበት! አንድ ብልቃጥ የጥፍር ቀለም ዓመት ተኩል የምታብቃቃ፣ ስቴክ የምትበላበት ከየት አምጥታ ነው! ይሄኔ አንዱን ሼባ ይዛ ይሆናል፡፡”
ሌላው ቡድን ዘንድ ደግሞ ምን ይባላል መሰላችሁ… “ስማ ያንን ችጋራም ምን እንደሚበላ አየኸው!” “ምንድነው የሚበላው?” “በእናትህ በቅዳሜ ምድር ክክ ምናምን ይበላል!” “የፈለገውን ቢበላ ምናለበት!” “የምን መፈለግ ነው! ችጋራም ነው እንጂ! የሚሠራው ቢዝነስ ቀላል መሰለህ! ልጄ ከሰዎቹ ጋር ተለጥፎ…” እናላችሁ…ልንመገብ ገብተን ስለሌሎች ተመጋቢዎች… “ከዕለታት አንድ ቀን…” ምናምን ታሪኮች የምናበዛ ሰዎች በርክተናል፡፡ የምር ግን…ነገሬ ብላችሁ እዩልኝማ…አሥር ጠረጴዛ ዘሎ ያሉ ሰዎች ያለ አጉሊ መነጽር እያሻገሩ አጎራረሳችሁንና አዋዋጣችሁን ‘ሲገመግሙ’ (ቂ…ቂ…ቂ…) እኔ የምለው…አጎራረሳችን የትኛው ካምፕ ውስጥ እንዳለን ያስነቃብናል እንዴ! ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… አዲስ አበባ በራሷ አነሳሽነት ነዋሪዎቿን ‘በመደብ’ እየለየች ነው፡፡
ልክ ነዋ…‘ንጥጥ’ ያሉ ሀብታሞች በተወሰኑ አካባቢዎች፣ ‘ምጥጥ’ ያሉ ቺስታዎች ደግሞ በየስርቻው! ሟርት አያስመስልብኝና እንዲህ አይነት ነገሮች እየበዙ በሄዱ ቁጥር የኋላ፣ ኋላ አሪፍ አይሆንም፡፡ ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…አሁን ‘የምንፈራው’ የሀብታሞቹን መኮሳተር (ለመኮሳተርስ ሲያዩን አይደል!) የጥበቃዎችን ግልምጫ ነው፡፡ ስሙኝማ…እግረ መንገዴን የሆነ ነገር ትዝ ብሎኝ ነው… አንዳንድ ሰዎች ‘መለዮ ሲለብሱና ዱላ ቢጤ መወዝወዝ ሲጀምሩ’ … አለ አይደል…የሚናፍቃቸው ዱላውን የሚያሳርፉበት ጀርባ ነው እንዴ! አሀ…በሰፈር ደረጃ ያሉ አንዳንዶቹን እኮ ስታዩዋቸው…አለ አይደል… በዓይናቸው እናንተን እያዩ በልባቸው… “ይሄ እንዲህ ትከሻውን እያሳየ የሚንጎማለለውን ቀልጥሞ፣ ቀልጥሞ መጣል ነበር!” እያሉ የሚያስቡ ይመስላችኋል፡፡
እና ‘መረጋጋት’ን የመሰለ ነገር የለም፡፡ ልክ ነዋ…ዱላው ‘እዛኛው እጅ’ ላይ የገባ ዕለት “…ይቅርታ እለምናለሁ፣ ጥፋቴን አውቄያለሁ…” ምናምን አይነት የአድማጮች ዘፈን ምርጫ አይሠራም! እኔ የምለው…ካወራን አይቀር…እዚቹ ከተማ ‘ጌትድ ኮሚዩኒቲስ’ የሚባሉ ግቢዎቹ ብቻ ሳይሆኑ ሙሉ መንደሮቹ ራሳቸው ግማሽ የእግር ኳስ ሜዳ በሚያካክሉ በሮች እየተከረቸሙ ነው፡፡ (ቀስ ብሎ ደግሞ ሙሉ አውራጃን ዓመት ሙሉ ቀጥ አድርገው ‘መቀለብ’ በሚችል ገንዘብ የሚገዙ መኪኖች በሚያልፉባቸው መንገዶች “ዝር ትሉና!” እንዳንባል መፍራት ነው!) እናላችሁ…ቀደም ሲል የመኖሪያ ግቢ በር ላይ ነው “ማንን ፈልገህ ነበር?” የምንባለው፡፡ አሁን ግን በታጠሩት መንደሮች ዋና በር ላይ ነው “ወዴት ነው!” የምንባለው፡፡ ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…በፊት እኮ የሀብታምና የድሀ መኖሪያ የሚለየው እንዲህ በመንደር ሳይሆን በቤቶቹ ትልቅነት ምናምን ነበር፡፡ እዚህ ጋ ቅልጥ ያለ ቺስታ እንደ ባለቤቷ ጠጅ ያንጋደዳት ጎጆ ውስጥ እየኖረ፣ ከፊት ለፊቱ ደግሞ የፊታውራሪ እከሌ የተንጣለለ ግቢ ይገኛል፡፡
(በነገራችን ላይ ፊትአውራሪ የሚለው መጠሪያ እየጠፋ መሄዱ የፊት አውራሪነት ባህሪይም አብሮ እየጠፋ ነው ማለት አይደለም፡፡ እንደውም ባይብስበት ነው!) እናላችሁ…ፈራንካው ያላቸው ሰዎች መንደሮቻቸውን በትላልቅ የብረት በሮች እንደሚዘጉት ሁሉ፣ ባለፈረንካዎችና ‘ባለድርሻ አካላቱ’ (ቂ…ቂ…ቂ…) በሁሉም በኩል ራሳቸውን በትላልቅ ‘የብረት በር’ እየከለከሉ ነው፡፡ ለምሳሌ…የፈረንካ ሰፈር ትኩስ ሀይሎች ሲገናኙ የሚያወሩት ምን ይመስለኛል መሰላችሁ… “ፌስቡክ ፍሬንዶቼ አራት ሺ ሰባት መቶ ሆኑ!” “ዋው! የእኔ ገና ሦስት ሺህ ናቸው፡፡ በቀደም ፍሬንድ የሆነችኝ…አንድ ምን የመሰለች ልጅ በፌስቡክ አግኝቻለሁ፡፡“ “ዩ ዶንት ሴይ! ከስቴትስ ነው?” “ኖ እዚሁ ነች…” “ኋት! ዩ ሚን ሺ’ዝ ሎካል!” “ብታያት እንዲህ አትልም ነበር፡፡ ምን የመሰለች ቺክ መሰለችህ! እንደውም ፕሮፋይል ፒክቸሯን ላሳይህ…” ከዛማ ሳምሰንግ ጋላክሲ ኤስ ፋይቭ ምናምን ይወጣል፡፡ ‘እዚህኛው ሰፈር’ ደግሞ ‘ፌስ’ ገና ከ‘ቡክ’ ጋር ሳይያያዝ ከሰው ልጅ አካል አንዱ የሆነበት ቺስታው መንደር ምን የሚባባሉ ይመስለኛል መሰላችሁ… “ስማ ከዚያች ልጅ ጋር እንዴት ናችሁ…” “የቷ!” “የቷ ትላለህ እንዴ! ያቺ ቀበሌ ሸማቾች ምናምን የምትሸጠው…” “ምን ታደርግ አንተ…እኔ ልጄ ስንት ሀሳብ አለብኝ! ሥራ ፍለጋ ስንከራተት ሁለት ዓመት እንዳለፈኝ አታውቅም!” “አትበሳጭ፣ ግዴለህም ለደግ ነው፡፡” “የምበላው እያጣሁ ለደግ…” ይልና መሀል ላይ ያቋርጣል፡፡ ‘ትርፍ’ ሊናገር ነበራ! አንድ ሁለቴ ያማትብና “…ይልቅ የማነበው አሮጌ መጽሐፍ ካለህ…” ምናምን እየተባለ ይቀጥላል፡፡እናላችሁ…እነሱ በ‘ቴክስት ሜሴጅ’ የፈለጉትን ቢባባሉ ያው የለመዱት ነው፡፡
እኛ ግን… አንዳንዱ የእኔ ቢጤ ‘ፋራ’ እንትናዬውን “ስዊቲ፣ አይ ላቭ ዩ ቬሪ ማች!” በሚል ሁሉም ሰው በሚገባው የፈረንጅ አፍ ግጥም አድርጎ ይጽፋል፡፡ አሀ…በእንግሊዝኛ ጥየቄ ማቅረብ ነገሩን ሁሉ ‘አሪፍ’ ያስመስለዋላ! ለነገሩ…“ስዊቲ!” “ሀኒ!” “ማይ ኤንጅል!” ምናምን ነገሮች በእኛ አፍ አያምሩማ! “ዳቦ ፍርፍር እየበሉ በእንግሊዘኛ ማወራት አያምርም…” የሚል ሰው የሆነ ቦታ ያለ አይመስላችሁም! (ስሙኝማ…አንዳንድ በፈረንጅኛ አፍ እንኳን የሚያነጥሱት ሰበሰቧቸው ቦታዎች ብቅ ማለታችን አይቀርም፡፡ እናላችሁ…በፈረንጅ አፍ ሲያወሩ ቋንቋው ላይ የሚያደርሱበት የኃይል ጥቃት ሶሪያና ኢራቅ አጠገብ ብንሆን ኖሮ ሌላ የዓለም ጦርነት ዋዜማ ሊሆን ይችል ነበር፡፡ አሀ… የአትክልት ተራ “ማዳም ጉድ ኦራንጅ…” አጠገብ እንኳን አይደርሱም! በዚህ ላይ ቅልጥ ያሉ ‘የብልግና’ ቃላት መሸለያ እየመሰላቸው ሲደጋግሙት ፈረንጅ ምን ያህል ይሳቀቅ ይሆን ያሰኛል! ከዓመታት በፊት በዕድሜ ‘ሲክስቲዋን’ ፉት ብለው ወደ ‘ሰቨንቲዋ’ የሚጠጉ እናት በ‘ታይታቸው’ ኋለኛ በኩል ‘ባይት ሚ’ (Bite me!) ተብሎ የተጻፈበት ለብሰው መሃል ከተማ ሲዘንጡ ማየቴ ትዝ ይለኛል፡፡ ብቻ ምን አለፋችሁ…በመንደር ትላልቅ በሮችም፣ በፌስቡክ ‘ፍሬንዶችም፣’ በ“ባይት ሚ” ምናምን አካሄዳችንም እያማረበት አይመስልም፡፡ የ‘ቦተሊካው’ ነገር አልበቃ ብሎ የሚለያዩን ነገሮች እየበዙ ሲሄዱ…አለ አይደል… ነገርዬው የትላልቅ በሮች ጉዳይ መሆኑ እንዳያበቃለት መፍራት ነው፡፡ከግቢ ‘በሮች’ ወደ መንደር ‘በሮች’…ተስፋ የሚሰጥ ‘ዕድገት’ አይደለም፡፡ ደህና ሰንብቱልኝማ!
ኢቦላ የላይቤሪያን ህልውና አደጋ ላይ ጥሎታል
- 160 ባለሙያዎች ህክምና ሲሰጡ በኢቦላ ተይዘው፣ ግማሽ ያህሉ ሞተዋል
- 2 ሺህ 46 ዜጎቿ በቫይረሱ ተይዘዋል፤ 1ሺህ 224 ሞተዋል
- የአገሪቱ አጠቃላይ እንቅስቃሴ ተቃውሷል
በላይቤሪያ በከፍተኛ ፍጥነት በመስፋፋት ላይ የሚገኘው የኢቦላ ቫይረስ፣ የአገሪቱን አጠቃላይ እንቅስቃሴ በማቃወስ ብሄራዊ ህልውናዋን አደጋ ላይ የጣለ ከፍተኛ ችግር የሆነበት አስከፊ ደረጃ ላይ መድረሱን ቢቢሲ ዘገበ፡፡የአገሪቱን የመከላከያ ሚኒስቴር ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ለ14 አመታት በዘለቀውና እ.ኤ.አ በ2003 በተቋጨው የእርስ በርስ ግጭት 250 ሺህ ያህል ዜጎቿ የሞቱባትና በመሰረተ ልማት አውታሮቿ ላይ ከፍተኛ ውድመት የደረሰባት ላይቤሪያ፣ አሁን ደግሞ ኢቦላ እንደ ሃገር መቀጠሏን ጥያቄ ውስጥ የሚከት የህልውና ፈተና ሆኖባታል፡፡ በቅርቡ በአገሪቱ የተቀሰቀሰው የኢቦላ በሽታ ከጊዜ ወደጊዜ በከፍተኛ ሁኔታ እየተስፋፋ መምጣቱን የጠቆመው ዘገባው፣ በበሽታው ከተጠቁ 2ሺህ 46 የአገሪቱ ዜጎች መካከል 1ሺህ 224 ያህሉ ተህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን ገልጧል፡፡“ኢቦላ ለላይቤሪያ ብሄራዊ ህልውና እጅግ አደገኛ ስጋት እየሆነ ነው፡፡ በፍጥነት በመሰራጨት ላይ የሚገኘው ይህ በቀላሉ የሚተላለፍ ገዳይ ቫይረስ፣ በአገሪቱ አጠቃላይ እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ ቀውስ ፈጥሯል፡፡” ብለዋል የላይቤሪያ የመከላከያ ሚኒስቴር ብሮዊን ሳሙካይ፣ ባለፈው ማክሰኞ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት አባላት ጋር ባደረጉት ውይይት፡፡
በሽታው በአገሪቱ ክፍተኛ ጥፋት እያደረሰ እንደሚገኝ የገለጹት ሚኒስትሩ፣ በቂ የጤና መሰረተ ልማት ያልተሟላላት የላይቤሪያ የጤና ተቋማት በበሽታው ተጠቂዎች መጣበባቸውንና ተገቢውን የህክምና አገልግሎት መስጠትና የቫይረሱን ስርጭት መግታት የማይቻልበት ደረጃ ላይ መደረሱን አስረድተዋል፡፡ አለማቀፉ ማህበረሰብ በላይቤሪያ ለተከሰተው የኢቦላ ችግር የሰጠው ምላሽ እጅግ አናሳ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ላይቤሪያ ከፍተኛ የሆነ የጤና መሰረተ ልማት አውታሮች፣ የህክምና ቁሳቁስ፣ የህክምና ባለሙያና የገንዘብ እጥረት እንዳለባት የገለጹት ሚኒስቴሩ፣ ይህም አገሪቱ በፍጥነት እየተሰራጨ ያለውን የኢቦላ በሽታ ለመግታት እንዳትችል እንዳደረጋት ተናግረዋል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የላይቤሪያ ልኡክ በበኩሉ፣ የአገሪቱ የህክምና መስጫ ተቋማት በተገቢው ሁኔታ ያልተደራጁ መሆናቸው በቂ ህክምና ለመስጠት አለማስቻሉን ገልጾ፣ ተገቢውን ስልጠና ሳይወስዱና ጥንቃቄ ሳያደርጉ የህክምና ስራቸውን ሲያከናውኑ የነበሩ 160 የጤና ባለሙያዎች በሽታው መያዛቸውንና ግማሽ ያህሉም ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን አስታውቋል፡፡ላይቤሪያ ችግሩ ከተከሰተባቸው ሌሎች የምዕራብ አፍሪካ አገራት ጋር ሲነጻጸር፣ በሽታውን በመግታት ረገድ ይህ ነው የሚባል ተጨባጭ ስራ አለመስራቷን ጠቆሞ፣ በቫይረሱ የተጠቁ ዜጎችን ለማከም በጤና ተቋማት የአልጋ እጥረት መኖሩንም ገልጧል፡፡የአለም የጤና ድርጅትም፣ በላይቤሪያ የተከሰተውን የኢቦላ በሽታ ችግር ለመፍታት ትኩረት ሰጥተው በመስራት ላይ ለሚገኙ አለማቀፍ ድርጅቶች፣ የጀመሩትን ጥረት በሶስትና አራት እጥፍ እንዲሳድጉ ጥሪ አቅርቧል፡፡
“ሊፋን ሞተርስ” ኢትዮጵያን የምሥራቅ አፍሪካ ማዕከል ሊያደርግ አቅዷል
ኢትዮጵያ ጦርነት የሌለባት ሰላማዊ አገር በመሆኗ፣ ሕዝቧም ቀማኛ፣ ዘራፊና ነጣቂ ባለመሆኑ ኢትዮጵያን የምሥራቅ አፍሪካ ማዕከል አድርገን እየሠራን ነው ሲሉ የሊፋን ሞተርስ ሥራ አስኪያጅ ሚ/ር ፍራንክ (በቻይናዊ ስማቸው ሊዩ ጂያንግ) ገለፁ፡፡ ሚ/ር ፍራንክ ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረጉት ቃለ - ምልልስ፤ “የኢትዮጵያ ሕዝብ ጨዋ ነው፣ ስርቆት፣ ዝርፊያ፣ቅሚያና ነጠቃ የለበትም፡፡ ለዚህም ሕዝቡን፣ ደንበኞቻችንንና መንግሥትን በጣም እናመሰግናለን” ብለዋል፡፡ ወደፊት ወደ ምሥራቅ አፍሪካ ጐረቤት አገራት የመኪና ምርቶችን ለመላክ ኢትዮጵያን ማዕከል አድርገው ለመስራት ማቀዳቸውን በመግለጽም በዱከም ኢስተርን ዞን፣ በ400 ሚሊዮን ዶላር ዘመናዊ የመኪና መገጣጠሚያ ፋብሪካ እየገነቡ እንደሆነ አስታውቀዋል፡፡ እስካሁን 3,500 መኪኖች መሸጣቸውን የጠቀሱት ሥራ አስኪያጁ፤ ወደፊት እንደገበያው ሁኔታ በዓመት 5,000 መኪኖችና ከዚያም በላይ ለመገጣጠም ማቀዳቸውን ገልፀዋል፡፡
የዘንድሮው የመኪና ሽያጭ ገበያ በተለያዩ ምክንያቶች የጠበቁትን ያህል ባይሆንም ወደፊት እንደሚሻሻል የጠቆሙት ኃላፊው፤ ለገበያው አለመጨመር ዋነኛው ችግር ኢትዮጵያውያን ከአዲስ መኪና ይልቅ አሮጌ መግዛት ስለሚወዱ ነው ብለዋል፡፡ “አሮጌ መኪና የመጠቀሚያ ጊዜ ወሰን ስለሌለው አሁን በጐዳና ላይ የሚታዩት አብዛኞቹ አሮጌ መኪኖች ከ30 ዓመት በላይ ያገለገሉ ናቸው፡፡ በዚህም የነሳ የተቃጠለ ጋዝ በመልቀቅ አካባቢን ይበክላሉ፤ ከፍተኛ የድምጽ ብክለት ይፈጥራሉ፣ የመኪና አደጋ የመፍጠር ሚናቸው ከፍተኛ ነው፡፡ ከዚህም በላይ የአረንጔዴ ልማት ኢኮኖሚ ፖሊሲን ስለሚፃረሩ መንግሥት ትኩረት ሊሰጠው ይገባል” ሲሉ አሳስበዋል፡፡ የውጭ ምንዛሪ ችግር እንዳለባቸው ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፤ “የውጭ ምንዛሪ ችግር የለብንም፤ ምክንያቱም እኛ ወኪል ሳንሆን በ160 አገሮች ቅርንጫፍ ያለው የቻይናው ሊፋን ግሩፕ አካል ነን፡፡ ስለዚህ የውጭ ምንዛሪ እጥረት ሲኖር፣ ሌሎች ድርጅቶች ከ6 እስከ 8 ወር ሲጠብቁ፣ እኛ ከ15 ቀንና ቢበዛ ከሁለት ወር በላይ አንጠብቅም፡፡ ትንሽ ችግር የገጠመን በኤክሳይዝ ታክስ ነው፡፡
ለእኛ የተለየና ስሌቱም ግልጽ ስላልሆነ ትንሽ ቅሬታ ፈጥሮብናል፡፡ ነገር ግን ከገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት፣ ከኢንዱስትሪና ከውጭ ሚ/ር መ/ቤቶች ጋር እየተነጋገርንና እየተወያየን ስለሆነ በቅርቡ ውሳኔ እንደሚያገኝ ተስፋ አለኝ” ብለዋል፡፡ የመኪና መገጣጠሚያ ፋብሪካዎች እየበዙ ስለሆነ ውድድሩን እንዴት ለመቋቋም እንዳሰቡ ተጠይቀው፤ “የመኪና መገጣጠሚያ ፋብሪካዎች መጨመር አያስጨንቀንም፡፡ ምክንያቱም፣ አንደኛ በኢትዮጵያ ገበያ ለመቆየት ወስነን ከፍተኛ ካፒታል እያፈሰስን ነው፡፡ ሁለተኛ፣ በዘመናዊ መኪና ደረጃ ሊፋን ኢትዮጵያ ገበያ ውስጥ በመግባት የመጀመሪያው ብራንድ ነን፡፡ ከሌላ ኩባንያ ጋር ሆነን ኢትዮጵያ የገባነው በ2007 ቢሆንም ከ2009 ጀምሮ ለብቻችን መገጣጠም በመጀመር፣ ከሕዝቡ፣ ከደንበኞችና ከመንግሥት ጋር እንዴት መሥራት እንዳለብን የ7 ዓመት ልምድ አካብተናል፡፡ “ሌላው ደግሞ መኪና መሸጥ ብቻ ሳይሆን ከሽያጭ በኋላ የእኛን ያህል ሰርቪስ የሚሰጥ እንደሌለ ደንበኞቻችን ይመሰክራሉ፡፡ ለሰርቪስ ከሚያስፈልጉ ነገሮች አንዱ መለዋወጫ ነው፡፡ ምንም ዓይነት እጥረት እንዳያጋጥም ለመለዋወጫ 10 ሚሊዮን ብር መድበናል፡፡ በእነዚህ ሁሉ ደንበኞቻችን ይመርጡናል ብለን እናምናለን” በማለት አስረድተዋል፡፡
“ዓመቱ ለኢንቨስትመንት አመቺ ይሆናል የሚል ተስፋ አለኝ”
- ዶ/ር አረጋ ይርዳው (የሚድሮክ ዋና ሥራ አስፈፃሚ)
በኩባንያችን በኩል ባለፈው አመት የተከናወኑት ተግባራት በሙሉ አመርቂ ነበሩ፡፡ በተለይ በቴክኖሎጂ ግሩፑ አካባቢ ጥሩ ስራ ነው የተሠራው፡፡ በቀጣይ ደግሞ በተለይ የመብራት አገልግሎቱ መሻሻልና የባቡር ዝርጋታው መጠናቀቅ፣ በሀገራችን ያለውን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ መልካም ያደርጉታል የሚል እምነት አለኝ፡፡ በአጠቃላይ 2007 እና ከዚያ በኋላ ያለው ዘመን ለኢንቨስትመንቱ አመቺ ይሆናል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ቴክኖሎጂ ግሩፑን በተመለከተ የወርቅ ምርት የመሳሰሉትን ሥራዎች እያስፋፋን ነው፡፡ የምናስፋፋበትም ምክንያት እስከዚያ መብራቱም ይደርሳል ብለን ስለምናስብ ነው፡፡ በአጠቃላይ በአገራችን የሚታየው ነገር ተስፋ ሰጪ ነው፡፡ በተረፈ ለኢትዮጵያ ህዝብ ዘመኑ የሰላም፣ የጤናና የብልጽግና እንዲሆን እመኛለሁ፡፡