Administrator

Administrator

400 ሺህ ፓውንድ ከመንግስት በጀት ወጪ አድርገው ነው የገዙት
    የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ፣ 400 ሺህ ፓውንድ የህዝብ ገንዘብ ወጪ በማድረግ ለአራት ሚስቶቻቸው 11 ዘመናዊ መኪኖችን ገዝተዋል በሚል የቀረበባቸውን ክስ የአገሪቱ ፍርድ ቤት ማጣራት መጀመሩ ተዘገበ፡፡ የህዝብ ገንዘብ ለግል ጥቅማቸው አውለዋል በሚል በተደጋጋሚ ሲከሰሱና ውሳኔ ሲተላለፍባቸው የከረሙት ዙማ፣ አሁን ደግሞ ይህን ያህል ገንዘብ አውጥተው ለሚስቶቻቸው የቅንጦት መኪና ገዝተዋል በሚል እንደተወነጀሉ የዘገበው ዘ ጋርዲያን፤መኪኖቹ ከአገሪቱ ፖሊስ በጀት ወጪ በተደረገ ገንዘብ መገዛታቸውን ጠቁሟል፡፡
የአገሪቱ የፖሊስ ሚኒስትር ንኮሲያንቲ ኔሊኮ ሰሞኑን መኪኖቹ መገዛታቸውን አምነው፣ ለፕሬዚዳንቱ ሚስቶች ደህንነት ሲባል ግዢው መፈጸሙ አግባብነት አለው ማለታቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡ ፍርድ ቤት ጉዳዩን እየተከታተለው እንደሚገኝም ተዘግቧል፡፡ ፕሬዚዳንቱ ለሚስቶቻቸው ገዟቸው ከተባሏቸው የቅንጦት መኪኖች ውስጥ አራት ሬንጅሮቨር ኤስዩቪ እና ሁለት ላንድሮቨር ዲስከቨሪ ኤስዩቪ የተባሉ እጅግ ዘመናዊ መኪኖች እንደሚገኙበትም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

የትርዒቱ ርዕስ፡ W@tch me…
ሠዓሊ፡ ቴዎድሮስ ሐጎስ
የትርዒቱ አይነት፡ የግል፤ የቀለም ቅብ ሥራዎች
ብዛት፡ ሃያ አራት
የቀረበበት ቦታ፡ አሊያንስ ኢትዮ-ፍራንሴስ፡ አዲስ አበባ
ጊዜ፡ ሚያዚያ 03-22፡2008 ዓ.ም
ዳሰሳ አቅራቢ፡ ሚፍታ ዘለቀ (የሥነ - ጥበብ አጋፋሪ)


እንደ መሻገሪያ
ልክ እንደ ወቅታዊ የሀገራችን እውነታ ሁሉ ሥነ - ጥበባችንም በበሰለና በተብላላ የግል የሥዕል ትርዒት አቅርቦት ድርቅ የተመታ እስኪመስል ነባራዊ መሰረት ይዞ፣ ዘመንን የሚተርክና ዘመን የሚሻገር ሃሳብና ክህሎት የሚታይበት ትርዒት በናፈቀኝ (ን) ወቅት ነበር ሠዓሊ ቴዎድሮስ ሐጎስ ‹W@tch me…›ን ይዞ ከተፍ ያለው፡፡  
ለነገሩ፤ የማሳያ ቦታዎች እጥረት፤ በወኔ የመነሳሳት፣ የሞራል፣ የመስሪያ ቦታ፣ የቁሳቁስና ባጠቃላይ የመኖር ዘዴ እጥረት፤ ብሎም በሚሰሩት የሥነ - ጥበብ ስራ የዕምነትና የፍልስፍና እጥረትና የመሳሰሉት ተግዳሮቶች የኢትዮጵያ ሥነ - ጥበብን ጋሬጣ የተሞላበት እንዲሆን ባደረጉበትና አብዛኛዎቹ ዘመነኛ ሠዓልያኖቻችን “የጥበብ መጀመሪያው ኤግዚቢሽን (በተለይ solo exhibition) መፍራት ነው!” የሚለውን ስላቅ እውነታ አድርገው የተቀበሉ በሚመስልበት በዚህ ወቅት ነው ሠዓሊ ቴዎድሮስ ‹የደረስኩበትን እንካችሁ!› ለማለት የደፈረው!
ይህ ዳሰሳ ግላዊ፣ ሃሳባዊና ሂሳዊ አተያዬን ለማንፀባረቅ፤ የትርዒት ዳሰሳ አናስራትን (elements) በጨረፍታም ቢሆን ለማስተዋወቅ የተጻፈ መሆኑንና ምንም ዓይነት ተቋማዊ መሰረትና ዝንባሌ እንደማይከተል ልገልጽ እወዳለሁ!!
*  * * *  *
ይመልከቱኝ …. (1)
የትርዒቱ ርዕስ በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተሰየመ፣ የተጻፈ ወይም የተነገረ ሲሆን W@tch me … የተሰኘ ነው፡፡ ይህ ስያሜ አማካይ የእንግሊዝኛ ቋንቋ ችሎታ ላለው ማንኛውም ሰው ውስብስብ አይደለም፡፡
ይመልከቱኝ … (2)
በትርዒቱ የቀረቡ ሁሉም ስራዎች “ይመልከቱኝ … ፤ እኔን ይመልከቱኝ …. እኔን ይመልከቱኝ እንጂ …” ማለት የሚፈልጉ ብቻ ሳይሆኑ እንድንመለከታቸው የሚያስገድዱ ጭምር ናቸው፡፡ እንዴት? ቢባል ዋነኛው ድርሰታዊ አወቃቀራቸው (Composition) ሲሆን የድርሰቱን ገዢ ቦታ በበላይነት ተቆጣጥረውት ነው የሚታዩትና የሚያዩን፡፡ በተጨማሪም ፊት ተደግነው (frontal ሆነው) የተደራሲን እይታዊ ንፍቅ (Visual inter-surface of the viewer’ን) እንዳይፈናፈን ወጥረው በመያዝ፣ ትኩረቱ ሁሉ እነሱ ላይ እንዲሆን ያስገድዱታል፡፡ ታዲያ ይህን ሁሉ አቅም ተጠቅመው ግዘፍ ከነሱ በኋላ ምን እንድናይና ምን አድርጉ ነው የሚሉን?
ብዙ ይላሉ፡፡ ለምሳሌ፡ ‹ይመልከቱን… እኛ አራታችንን …!!!› ይላሉ፡፡
ከትርዒቱ አዳራሽ መግቢያ በስተግራ ያለው ግድግዳ፣ የሁለት አንጋፋ ሰዓልያን የፊት ገጽ (portrait) የተሳለባቸውና እያንዳንዳቸው መቶ ሰማንያ በመቶ ሃያ ሴንቲ ሜትር አውታር ያላቸው ሁለት ስራዎች ተንጠልጥለውበታል፡፡
(ግድግዳው ከዘመናት በፊት ከብርቱ ደንጊያ የታነጸ በመሆኑ እንጂ ሁለቱ ስራዎች እንደተሸከሙት የሀሳብ ክብደት ቢሆን ግን ገና አንደኛው ስራ ሊሰቀልበት ሲሞክር ተብረክርኮና ተፈረካክሶ የእንቧይ ካብ ሆኖ ይቀር ነበር)፡፡ ቴዎድሮስ ለነዚህ ስራዎቹ ዓይነ - ግብ (Subject - matter) ያደረጋቸው ሁለቱ አንጋፋ ሠዓልያን፣ ሠዓሊ ታደሰ መስፍንና ሠዓሊ መዝገቡ ተሰማ ናቸው፡፡
እኒህ ሁለት ልሂቀ ጠበብት፤ ዘመናዊው የኢትዮጵያ ሥነ - ጥበብ ገና በሁለት እግሩ ለመቆም ደፋ ቀና በሚልበት ዘመን፣ አብዮት ፈንድታ ቋንጃውን መበጠስ ከጀመረችበት ከ1960ዎቹ አንስቶ እስከ አሁኑ ገና አቅጣጫውን መወሰን ካቃተው ዘመነኛዊው የኢትዮጵያ ሥነ-ጥበብ ትንታግ ድረስ ተመስጦአቸውን ሳያደፈርሱ፣ ጥናታቸውን ሳያቋርጡ፣ ባሕር ሃሳባቸውንና ጥልቅ እውቀታቸውን ሳይሰስቱ ለተማሪዎቻቸው ሲለግሱ፣ ትውልድ ሲገነቡና ራሳቸውን ሲወልዱ የኖሩ ብርቅዬና የቁርጥ ቀን የሀገር ልጆች ናቸው፡፡
 ድንብርብሩ እየወጣ አንዱን ሲይዝ ሌላውን እየለቀቀ በመጓዝ ላይ ባለው የስነ ጥበባችን ታሪክ ውስጥም አንዳችም ሳይረበሹ ይልቁንስ አቅጣጫቸውን እያጠሩ የሚጓዙት እኒህ አንጋፋ ሰዓልያን፤ የደረሱበትን ከፍታ አጥንቶ ተገቢው ቦታ ሊሰጣቸው ባልተቻለበት ሁኔታ በምስላዊ (figurative art) የሄዱበትን ርቀት ለመዘከር እንኳ ልብ በጠፋበት ዘመን ነው ቴዎድሮስ ከሃያ ስምንት ሳንቲ ሜትር የማትበልጥ ረቂቅ የፊት ገጻቸውን በዚያ ግዙፍ ሸራ ላይ ያለ ስስት እንዲናኙ፣ እንዲገዝፉና እንዲንፏለሉ ያደረገው፡፡ ከዚህ የላቀ አክብሮትና ዋጋ ለሁለቱ አንጋፋ ሠዓልያን የትም ተችሮ  አያውቅም! ታዲያ “ይመልከቱ … ይመልከቱ እንጂ … ማለት ይህ ነው ‘ንጂ! ደግ ያደረግህ ቴዎድሮስ!
ከአንጋፋውያኑ ሰዓልያን ትይዩ ደግሞ በተመሳሳይ ጥልቀትና አውታር እንዲሁ በሀገራችን የዘመናችን የሥነ - ጥበብ ፎቶግራፍ ፋና ወጊና ቀድሞ ሰዓሊ የነበረው ሚካኤል ጸጋዬ፤ እንዲሁም በዓለም-ዓቀፉ የሥነ-ጥበብ መድረክ ዘመንኛዊውን የኢትዮጵያ ሥነ-ጥበብ እያስጠራ ያለውን ሠዓሊ ዳዊት አበበ በግዝፈት አስቀምጧቸዋል፡፡ በገለልተኛው የሥነ-ጥበብ ታሪካችን ቅብብሎሹን በማስቀጠል ጉልህ ሚና እየተጫወቱ ካሉ ጥቂት ወጣት ሠዓልያን መሃል ሁለቱን መርጦ መሳሉ፣ ቦታ መስጠቱና የሚጠብቃቸውንም ኃላፊነት ማመላከቱ ሌላኛው የቴዎድሮስ ሐጎስ ‹ይመልከቱ› …. ነው ባይ ነኝ፡፡
ይመልከቱኝ … (3)
የፊት ገጽ እንደ አንድ የሥነ - ጥበብ ዘዬ ስንመለከተው፤ ጥንታዊ መሰረት ያለውና እስከ አሁኑ ጊዜም በስፋት የሚሰራበት ዘዬ ነው፡፡ ለምሳሌ ከጥንታዊት ግብጽ ሥነ - ጥበብ፣ ከጣሊያን ሬኔይሳንስ፣ ከመካከለኛው የአውሮፓ ሥነ - ጥበብ ከፍታ እስከ ዘመንኛ ፎቶግራፍ በሰፊው ጥቅም ላይ ውሏል፡፡ በዓይነትም ቢሆን ከሃይማኖታዊ፣ ታሪካዊ፣ የታዋቂ ሰዎች፣ የእርቃን፣ የተራና ተርታ ሰዎችን የፊት ገጽ የመስራት ዘዬ በሥነ - ጥበብ ታሪክ ውስጥ ተጠቃሽ ናቸው፡፡ በዓለም ታሪክም እንደነ ሊዎናርዶ ዳቬንቺ፣ ሬምብራንት፣ቪንሴን ቫን ጎ፣ ፓብሎ ፒካሶን የመሳሰሉ ስመ ጥር የዓለም ሠዓልያንም የፊት ገጽ በመስራት ይታወቃሉ፡፡
ቴዎድሮስ ሐጎስ፤ በዚህ ዘዬ ከአስር ዓመት በላይ ከመስራቱም ባሻገር ምናልባትም የራሱን ዘዬ በማዳበር፣ ስራዎቹ ጥልቀት እንዲኖራቸው በመመራመርና ሃሳቡን በማጠናከር ረገድ ግንባር ቀደም ዘመንኛ ሠዓሊያችን ነው ማለት እችላለሁ፡፡ ቴዎድሮስ የራሱን ዘዬ አዳብሯል? አዎ! ይህን ደግሞ ማየት የምንችለው የሚሰራቸውን ሰዎች የፊት ገጽ ከእውነታ አግዝፎ (larger than life size) ነው የሚሰራቸው፡፡ ከእውነታ አግዝፎ መስራት አዲስ ነገር ባይሆንም በእያንዳንዱ ስራዎቹ ይህንን የሙጥኝ ብሎ መስራቱ ዘዬውን ለማዳበር ረድቶታል፡፡
 በዚህ ትርዒት ከቀረቡ ስራዎች ሶስት አራተኛዎቹ ሞዴሎቹ የቀን ሰራተኞች ናቸው፡፡
የቀን ሰራተኞች እንደ ዓይነ - ግብ (Subject matter) መጠቀሙ ራሱን የቻለ ውሳኔና ድንጋጌ ነው፡፡ የቀን ሰራተኞች በአሁኗና በግንባታዎች አማካኝነት ዘመንኛ ለመሆን በምትጣጣረው ኢትዮጵያችን ያላቸውን ሚና ማንም አይዘነጋውም፡፡ ቴዎድሮስ ይህንን ሃቅ ከፊታቸው ይመልከቱ … እያለን ይመስለኛል፡፡
አለም አላለም ግን ሠዓሊው እንካችሁ ያለውን ተመልካቹ የመጠየቅ፣የመመርመርና የማዛመድ መነሳሳት ቢኖረው፣ ሠዓሊውን ከመረዳት አልፎ ለግል አስተሳሰቡና ለግንዛቤው የሚጠቅሙ አያሌ መንገዶችን መፍጠር ይችላል ባይ ነኝ፡፡ ደግሞ ምንስ ቢሆን የእነዚህ የኅብረተሰብ ክፍሎችን አኗኗርና አመለካከትን መመልከት የለብንም? ከ“ይመልከቱ” … ብዙ ነገር ማየት ይቻላል፡፡ ሌላው እንደ ዓይነ - ግብ (Subject matter) የተጠቀማቸው የቀን ሰራተኞች የለበሱት ልብስና በልብሶቹ ላይ የታተሙት ጽሁፎች ነው፡፡
ቴዎድሮስ እንደነገረኝ ከሆነ፣ በልብሶቹ ላይ የታተሙት ጽሁፎችን ትርጓሜ ለባሾቹ አያውቁትም፣ አያስጨንቃቸውምም፡፡ ይህ ደግሞ በሰፊው ህዝብም የሚስተዋል ነው፡፡
ይህንን ከአያሌ ጥያቄዎች ጋር ማገናኘት ይቻላል፡፡ ለምሳሌ ግሎባላይዜሽን የሀገርና የግለሰብ ማንነት ላይ ሊያደርሰው የሚችለው ተጽዕኖ፤ ተጽዕኖዎቹን ለመቋቋምም ሆነ በተጽዕኖዎቹ ስር ለመውደቅ እንደ ሀገርና ግለሰብ የገነባነው ማንነት ምን ያህል ዋጋ እንዳለው ለማሰላሰል ያስችሉናል፡፡
ምናልባት የመጨረሻ “ይመልከቱ”… የአንዳንድ ሞዴሎቹ አቋቋም፡
አቋቋማቸው ከትከሻቸው ዞር ያሉ፣ እይታቸውን ወደ ተመልካችና ወደ ሩቅ ያደረጉ ሰዎችን እንደ ሞዴል ተጠቅሟል፡፡
እንዲህ አይነት አቋቋሞች በአብዛኛው ልበ ሙሉነትን፣ ሩቅ አላሚነትን፣ ተስፈኝነትንና ታላቅነትን አመላካች ናቸው፡፡
ከነዚህም መሃል አንደኛውን የሥዕል መስሪያ ቀለም፣ ሌላኛውን ደግሞ በአንድ እጁ ደብተር በሌላኛው እጁ ሹራብ አንጠልጥሎ ሰርቷቸዋል፡፡ … ቀለምና ደብተር ምንን ይወክላሉ? ለምን ሌላ ነገር አልያስያዛቸውም?
እንደው ሳስበው  W@tch me…. ን መዳሰስ ብቀጥል ይመልከቱኝ … እያልኩ ላተክናችሁ ነው፡፡ ስለዚህ ይብቃኝ፡፡ እስቲ እናንተም የበኩላችሁን … በሉኝ! ቸር እንሰንብት፡፡

3.5 ሚሊዮን ፓውንድ እንደሚያወጡ ይገመታል

    ብራዚላዊው የእግር ኳስ ንጉስ ፔሌ፤ በተጫዋችነት ዘመኑ የተሸለማቸውና ይጠቀምባቸው የነበሩ የተለያዩ ውድ ንብረቶች በመጪው ወር ለንደን ውስጥ በሚካሄድ ጨረታ ለሽያጭ እንደሚቀርቡና 3.5 ሚሊዮን ፓውንድ ያወጣሉ ተብሎ እንደሚገመት ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ጁሊየንስ ኦክሽን በተባለው አጫራች ኩባንያ አማካይነት ለጨረታ ከሚቀርቡት የፔሌ ውድ ንብረቶች መካከል ዋንጫዎች፣ ውድ የእጅ ሰዓቶች፣ ሜዳሊያዎች፣ ኳሶችና ሌሎች የስፖርት ቁሳቁስ ይገኙበታል ያለው ዘገባው፣ ተጫዋቹ ከሽያጩ ከሚገኘው ገቢ የተወሰነውን በብራዚል ለሚገኝ አንድ የልብ ህክምና ሆስፒታል በስጦታ ለማበርከት ማቀዱን ገልጿል፡፡
ለጨረታው ከቀረቡት እቃዎች መካከል በዓለም እግር ኳስ ዋንጫ ቅርጽ የተሰራው የፔሌ ውድ ዋንጫ፣ እስከ 420 ሺህ ፓውንድ ያወጣል ተብሎ እንደሚገመት የጠቆመው ዘገባው፣ ሜዳሊያዎቹ 141 ሺህ ፓውንድ፣ 1ሺኛዋን ጎሉን ያስቆጠረባት ታሪካዊት ኳስም 42 ሺህ ፓውንድ ይሸጣሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ አመልክቷል፡፡
የ75 አመቱ ብራዚላዊ የእግር ኳስ ኮከብ ፔሌ፤ በአለማችን እግር ኳስ ታሪክ ደማቅ ተግባር የፈጸመ፣ ዘመን የማይሽረው ተጫዋች እንደሆነ የገለጸው ዘገባው፣ “የክፍለ ዘመኑ የዓለማችን ምርጥ የእግር ኳስ ተጫዋች” በሚል በፊፋ መሸለሙንም አስታውሷል፡፡

    ሰሞኑን ኢትዮጵያን የጎበኙት የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፊሊፕ ሃሞንድ፣ በሽብር ወንጀል ተከስሰው ሞት የተፈረደባቸውና በእስር ላይ የሚገኙት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ፤ የህግ ድጋፍ የሚያደርግላቸው ጠበቃ ማቆም ይችላሉ የሚል ማረጋገጫ ከኢትዮጵያ መንግስት እንዳገኙ ተገለጸ፡፡
ሪፕራይቭ የተባለው የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ተቋም በበኩሉ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ አንዳርጋቸው ከእስር ተፈትተው ከቤተሰቦቻቸው ጋር እንዲገናኙ የኢትዮጵያን መንግስት አልጠየቁም በሚል ትችት ሰንዝሮባቸዋል፡፡
ባለፈው ረቡዕ ኢትዮጵያን የጎበኙት ፊሊፕ ሃሞንድ፤ የአቶ አንዳርጋቸውን ጉዳይ በጉብኝታቸው ዋና አጀንዳ እንዳደረጉት የጠቆመው የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መግለጫ፣ ከጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝና ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ጋር በአቶ አንዳርጋቸው ጉዳይ ዙሪያ መምከራቸውንና አቶ አንዳርጋቸው ጠበቃ ማቆም እንደሚችሉ ማረጋገጫ እንደተሰጣቸውም ገልጧል፡፡
ፊሊፕ ሃሞንድ ምንም እንኳን አቶ አንዳርጋቸውን የእንግሊዝ ቆንስላ እንዲጎበኛቸው መፈቀዱና ወደ ፌደራል እስር ቤት እንዲዛወሩ መደረጋቸው አንድ እርምጃ ቢሆንም፣ ሌሎች ቀጣይ እርምጃዎች መወሰድ አለባቸው ሲሉ ለጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለ ማርያም መግለጻቸውንና፣ የህግ አማካሪ እንዲኖራቸው መፈቀዱን ተናግረዋል፡፡
እንግሊዝ በሌሎች አገራት የፍትህ ስርዓት ጣልቃ እንደማትገባ የገለጹት ፍሊፕ ሃሞንድ፤ የአገሪቱ ቆንስላ የአቶ አንዳርጋቸውን  ደህንነትና የህግ ምክር አገልግሎት ማግኘት የማረጋገጥ ሚናውን እንደሚጫወት ጠቁመው መንግስታቸው ግለሰቡንና ቤተሰቦቻቸውን መርዳቱን  እንደሚቀጥል አስታውቀዋል፡፡
የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ከፍተኛ ባለስልጣን ባለፈው ረቡዕ አቶ አንዳርጋቸውን እስር ቤት ሄደው መጎብኘታቸውንም መግለጫው አክሎ ገልጧል፡፡
ሪፕራይቭ የተባለው የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ተቋም ከትናንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ፤ “ፊሊፕ ሃሞንድ ጉብኝታቸው የፈጠረላቸውን መልካም አጋጣሚ አልተጠቀሙበትም፤ አቶ አንዳርጋቸው የህግ ድጋፍ የሚያገኙበትን ሁኔታ ፈጥሪያለሁ ማለቱም ትርጉም የለውም” በማለት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሩን መግለጫ አጣጥሎታል፡፡

የግብጽ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሜን ሹክሪ፤ “የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ እውን ሆኗል፣ ህልውናውን ለመካድ መሞከር ራስን መሸንገል ነው፤ በተጨባጭ የምናየውን ግድብ ህልውና ለመካድ መሞከር አያዋጣንም” ማለታቸውን አሃራም የተባለው የአገሪቱ ድረገጽ ዘገበ፡፡
ሚኒስትሩ ባለፈው ማክሰኞ አል-ሃያት በተባለው የአገሪቱ የቴሌቪዥን ጣቢያ ባደረጉት ንግግር፣ አገሪቱ የግድቡን ጉዳይ በተመለከተ የምታደርገው እንቅስቃሴ በጥርጣሬ፣ ባለመተማመንና በተጋነኑ አደጋዎች ላይ የተመሰረተ አለመሆኑን ጠቁመው፣ ይሄም ሆኖ ግን ከግድቡ ጋር በተያያዘ ለአገሪቱ አስጊ የሆኑ አደጋዎች መኖራቸውን አስታውቀዋል፡፡
መንግስታቸው እነዚህ አደጋዎች በአገሪቱ ላይ ምንም አይነት ጉዳት የማያደርሱበትን መላ ለመፍጠር የሚያስችል ስምምነት ለመፈጸም ከኢትዮጵያና ከሱዳን ጋር ውይይት እያደረገ እንደሚገኝ ሚኒስትሩ ቢናገሩም፣ የአደጋዎቹን ባህሪና ምንነት በተመለከተ ግን ግልጽ ማብራሪያ አለመስጠታቸውን ዘገባው ጠቁሟል፡፡

    ለ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና መቋረጥ ምክንያት የሆነውን የፈተና መሰረቅ ጉዳይ ፖሊስ እየመረመረ መሆኑ የተገለፀ ሲሆን ለድጋሚ ፈተና የህትመትና የመጠረዝ ስራ እየተከናወነ ነው ተብሏል፡፡
በስርቆቱ ጉዳይ የሚደረገው ምርመራ በተጠናከረ መልኩ ሙሉ ለሙሉ በፀጥታ ኃይሎች መያዙን ያስታወቁት በትምህርት ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አህመድ ሲራጅ፤ ጉዳዩን ተከታትሎ ለህግ የማቅረብ ስራ የፖሊስ መሆኑን ጠቁመው ጉዳዩ የፀጥታ አካላት የሚፈትኑበት ነው ብለዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ አዲስ አድማስ ያነጋገራቸው የህግ ባለሙያ፤ በመንግስት ከፍተኛ መስሪያ ቤት እንዲህ ያለው ወንጀል ሲያጋጥም ፖሊስ በሁለት መንገድ ምርጫ ሊያደርግ እንደሚችል ጠቅሰው አንደኛ ቀጥታ ጥቆማ ከመስሪያ ቤቱ ሲደርሰው፣ ጥቆማ ካልደረሰው ያገኘውን ፍንጭ መነሻ አድርጎ ምርመራ እንደሚያደርግ አብራርተው፤ ማህበራዊ ድረ ገፅ ላይ “ፈተናው ተሰርቋል” ተብሎ ይፋ በተደረገ ጊዜ ፖሊስ ምን ህል ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ ምርመራ ለማድረግ እንደሞከረ መጠየቅ አለበት ብለዋል፡፡ ትምሀርት ሚኒስቴር በበኩሉ፤ በአሁን ወቅት በዋናነት ትኩረት የሰጠው ፈተናው በድጋሚ በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ በጥንቃቄ ማካሄድ በሚቻልበት ጉዳይ ላይ መሆኑን የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
ቀደም ሲል ፈተናው ተጠርዞ፣ ታሽጎ፣ በሀገሪቱ በሚገኙ 802 የፈተና ጣቢያዎችና በውጭ ሀገር በሚገኙ 3 ጣቢያዎች ለማድረስ እስከ 3 ወር ይፈጅ እንደነበርና የተዘጋጀው መጠባበቂያ ፈተና በልዩ ግብረ ኃይል እየተመራ፣ ከፍተኛ ርብርብ በማድረግ በ23 ቀን ውስጥ ሁሉንም ጉዳዮች ለማጠናቀቅ ጥረት እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡
ፈተናውን ለመስጠት የታቀደው ከሰኔ 22 እስከ 30 ባለው ጊዜ ውስጥ ሲሆን የረመዳን የፆም ወቅት መሆኑንና የኢድአል ፈጥር በአልም ከተያዙት ቀናት መካከል በአንዱ ሊሆን እንደሚችል በመግለፅ የተያዘው ፕሮግራም እንዲቀየር እየተጠየቀ ቢሆንም ትምህርት ሚኒስቴር ፕሮግራሙን እንደማይቀይር አስታውቋል፡፡
ፈተናው ተሰርቆ መውጣቱ ተረጋግጦ ቀደም ያለው መርሃ ግብር ከተሰረዘ በኋላ በአጭር ጊዜ ውስጥ ፈተናውን እንዴት መስጠት ይቻላል በሚለው ላይ አመራሮችና ባለሙያዎች ውይይት ማድረጋቸውን ሃላፊው ጠቁመው፤ በ23 ቀናት ውስጥ ማከናወን እንደሚቻል ታምኖበት ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴ መገባቱን ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል ይሄም የተማሪዎችን የጭንቀትና የመቆዘሚያ ጊዜ ለመቀነስ ታስቦ ነው” ገልፀዋል - ይሄም፡፡
የረመዳን ወር መሆኑ እንደሚታወቅና ካለው ችግር አንፃር በአሉ የሚውልበትን ቀን መዝለሉ አማራጭ ሆኖ መገኘቱን ያብራሩት ኃላፊው የረመዳንን ወር “ፆም ከስራ ጋር የታረቀ  ህብረተሰብ በስራ የሚያሳልፈው መሆኑን ሙስሊሙ ህብረተሰብም መንግስት ያለበትን ጫና በአግባቡ ይረዳል የሚል እምነት እንዳለ ተናግረዋል፡፡ አሁን በድጋሚ ከተያዘው ቀን ወደፊት ይራዘም ቢባል የፈተና ማረሚያ፣ ውጤት ማሳወቂያና የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ፕሮግራሞችን የሚያፋልስ መሆኑን ያስረዱት ኃላፊው አስቀድሞ የተያዘውን የጊዜ ሰሌዳ ለማሳካት ሲባል ርብርብ ማድረጉ አስፈላጊ ሆኗል ብለዋል፡፡

     የኦስካር ተሸላሚዋ የፊልም ተዋናይት አንጀሊና ጆሊ በታዋቂው የለንደን ስኩል ኦፍ ኢኮኖሚክስ በቀጣዩ አመት በሚጀመረው የሁለተኛ ዲግሪ ፕሮግራም የሴቶች፣ የሰላምና የደህንነት ኮርስ ተጋባዥ መምህርት ሆና ለማስተማር መመረጧን ዩኒቨርሲቲው አስታወቀ፡፡የፊልም ተዋናይቷ ከታዋቂዎቹ የእንግሊዝ ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ በሆነው የለንደን ስኩል ኦፍ ኢኮኖሚክስ ከሴቶች፣ ከሰላም፣ ከደህንነት፣ ከሰብዓዊ መብቶችና ከጾታ ጋር የተገናኙ ጉዳዮችን ከማስተማር በተጨማሪ፣ በተለያዩ ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ንግግር እንደምታደርግ፣በአውደጥናቶችና በህዝባዊ ዝግጅቶች ላይም እንደምትሳተፍ ታውቋል፡፡
 “ተማሪዎችን ለማስተማርና ከእነሱም ለመማር ጓጉቻለሁ” ያለቺው አንጀሊና ጆሊ፣ከተማሪዎቿ ጋር ልምዶችን እንደምትለዋወጥና በጉዳዩ ዙሪያ ከተለያዩ የአለማችን አገራት መንግስታትና ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጋር በትብብር እንደምትሰራም ገልጻለች፡፡
አንጀሊና ጆሊ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ተቋም የበጎ ምግባር አምባሳደርና ልዩ መልዕክተኛ ከመሆኗ በተጨማሪ በአለማቀፍ ደረጃ በሚከናወኑ የሴቶች የመብት ጥሰቶች፣ ጾታዊ ጥቃቶች፣ የህጻናት ደህንነት እንክብካቤዎችና በሌሎች የበጎ ምግባር እንቅስቃሴዎች ላይ በመሳተፍ ትታወቃለች፡፡

Monday, 30 May 2016 09:22

የፍትሕ ኤልኒኖ!

   ከብዙ የሃሳብ መንሸራሸር በኋላ የቢሮ ኃላፊው ጠንከር ያለ አስተያየት ሰጡ፡፡ ‹‹ታውቃላችሁ? እኛ የምንነጋገረው የቢሮአችንን፣ የአገራችንን እንዲሁም የመንግስታችንን ጥቅም በሚያስከብር ጉዳይ ነው፡፡ በእርግጠኝነት ይህቺ ሴት ለዚህ ቢሮም ሆነ ለአገራችን  እድገትና ትራንስፎርሜሽን የማታስፈልግ ናት ብል ማጋነን አይሆንብኝም፡፡ እሷ እኮ ሌላው ቢቀር ለመንግስት ፖሊሲና ስትራቴጂ እንኳን ደንታ የሌላት፣ የአመለካከት ችግር ያለባትና ልማት አደናቃፊ ሴት ነች›› አሉ፡፡
ለዛሬው የጭንቅ አጀንዳቸው መንስኤዋ ኤፍራታ ይመር ናት፡፡ ኤፍራታ ቀውላላ ቁመት፣ ረጂም ጸጉር፣ ንጹህ ልብ፣ ብሩህ አዕምሮ የታደለች የ31 ዓመት ልጅ እግር ናት፡፡ እልኸኛ ከመሆኗ በተጨማሪ መበለጥን አብዝታ ትጠላለች፡፡ ተማሪ እያለች የምትናደደው በመሳሳቷ ሳይሆን በሌላ ተማሪ ከተበለጠች ነበር፡፡ ብዙ ማውራትም ሆነ ከወንዶች ጋር መቀለድ አትፈልግም፡፡ ከባሏም ጋር የተፋታችበት ምክንያት አቋም የሌለውና ልክስክስ መሆኑን በመረጃ ከደረሰችበት በኋላ ነበር፡፡ ትክክል አለመሆኑን ብታውቅም የስልክ ጥሪዎችን በመቅረጽም ሆነ ሰነዶችን ‹‹ኮፒ›› በማድረግ ማንም አይደርስባትም፡፡፡ የዛሬን ፍቅር ሳይሆን የነገን ማሰብ ይበጃል ትላለች፡፡ ሲበዛ ጠንቃቃና ለቃሏ ታማኝ ነች፡፡ ‹‹ክርስቶስን አደርገዋለሁ!›› ብላ የማለችበትን ነገር ሳታደርግ አታፈገፍግም፡፡
የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተሩ ኤልያስ፤ቦርጩን እያሻሸ  ራሱን ከፍ ዝቅ በማድረግ በአድናቆት ጭምር የሀሳቡን ትክክለኝነት አረጋገጠ፡፡ የቢሮ ኃላፊው የሁሉንም ስሜት ለመረዳት ወደ ሌሎቹ አማተረ፡፡
የፋይናንስ አስተዳደሩም፤‹‹ልክ ነው›› ለማለት ራሱን ነቀነቀ፡፡ የግዢ አስተዳደሩ ጉሮሮውን ጠራርጎ፣ተንኮለኛ ዓይኑን እያጉረጠረጠ፤‹‹ልክ ነው›› አለ፡፡ ‹‹ግን ሴትዮዋ አደገኛ ናት፡፡ የሆነ ነገር ካልተደረገች ሌላ መዘዝ ማምጣቷ አይቀርም፡፡ መቼም ድርቅናዋንና ሐቀኝነቷን ሁላችንም እናውቀዋለን›› ብሎ ማብራራት ከጀመረ በኋላ፣ደጋፊዋ ነህ እንዳይባል ስለሰጋ መልሶ ተወው፡፡
የቢሮ ኃላፊው ቀብረር ብሎ፤‹‹ምንም አታመጣም አትስጉ፡፡ አሁን በተወያየንበት ጉዳይ  ከተስማማን፣ በተነጋገርነው መሰረት ቃለ-ጉባዔውን እንፈራረምበት፡፡ ከዚያም በኋላ በራሷ ወጥመድ ስትታነቅ ሁሉም ነገር ይገባታል፡፡ አይደለም ውሰጂ የተባለችውን ሲሳይ ይቅርና ኪስ ማውለቅ ትጀምራለች፡፡›› አለ የምጸት ሳቅ እየሳቀ፡፡ እነሱም አብረው ሳቁ፡፡
የቢሮ ኃላፊው ሲያወራ  ባያስቅም መሳቅ፣ ሳይገባቸው  የገባቸው ለመምሰል ራሳቸውን መነቅነቅ የዘወትር ተግባራቸው ነው፡፡
      የቢሮ ኃላፊው የፖለቲካ ሹም ከመሆኑም ባሻገር ብዙ ገንዘብ የሰበሰበ በመሆኑ በቅርበት የሚያውቁት ‹‹እጁ ረጂም ነው›› ይሉታል፡፡
 በየትኛውም መንገድ ቢመጡበት መውጫ ቀዳዳ አለማጣቱ ብቻ ሳይሆን ነገር አዋቂና የፈለገውን መጥቀም፣ የፈለገውን መጉዳት የሚችል ሰው በመሆኑ ጭምር ነው፡፡ ሌላው ልዩ የሚያደርገው ነገር በሚሊዮን ብር እያፈሰ በአካውንቱ ውስጥ እዚህ ግባ የሚባል ብር አለመገኘቱ ነው፡፡ በየትኛው አካውንት የትኛው ባንክ ያስገባው ወይም ቆፍሮ ይቅበረው፣ በውጪ ዓለም ባሉ ባንኮች ያሽሸው እስካሁን የሚታወቅ ምስጢር የለም፡፡
     ጉቦ ሲቀበልም በጣም ጠንቃቃ ከመሆኑ የተነሳ፣ የሚቀበለው በጥሬ ብር በሚያምነው ሰው አማካኝነት  ብቻ ነው፡፡ አለዚያም ለሆነ ሰው፣ በሆነ ስም፣ ከሆነ ሰው፣ ወደሆነ ሰው፣ ለሌላ ሰው፣ በሌላ ሰው ስም ይደርሰዋል እንጂ በቼክ ወይም በአካውንቱ ብር ፈጽሞ አይቀበልም፡፡
በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠር ብር የሚፈርምበት አጋጣሚ ካለ፣ ስብሰባ ወይም ሌላ ምክንያት ፈጥሮ ወክሎ ይጠፋል፡፡ ሁሉንም ነገር በስልክ በወከለው ሰው አማካኝነት ‹‹ፈርምላቸው፤እንዲህ አድርገው…›› እያለ  በማስፈጸም ራሱን ነጻ ለማድረግ ሁሌም የተዘጋጀ  ክፉ ሰው ነው፡፡ ትልቁ  ብልጠቱ ደግሞ የሚገባውን ነገር ለሚገባው ሰው አለመንፈጉ ነው፡፡ አብዛኛው ሰው የሚያደንቀው ግን ሁሉንም ቤተሰቦቹን ከድህነት አረንቋ ማውጣት የቻለ ጀግና በመሆኑ ነው፡፡ ዘመድ ቤተሰቡ ይቅርና ሰፈርተኛውም እንደ ዓይናቸው ብሌን ይጠነቀቁለታል፡፡ ተቸገርኩ ብሎ የመጣን ሰው አይመልስም፡፡ ማንን ይዞ ከማን ጋር መሥራት እንዳለበት ጠንቅቆ የሚያውቅ መሰሪ ነው፡፡  አሁን አሁንማ ሰዎች አሰራሩን ከእሱ የበለጠ የተረዱት ይመስላሉ፡፡
   ሁሉም የሥራ ኃላፊዎች ሀሳብ ከመስጠት ይልቅ የእሱን ሀሳብ በማድነቅ እንደ ወትሮው አጸደቁ፡፡ ቃለ ጉባዔውን እየተፈራረሙ ሳለ ምንም ሀሳብ ያልሰነዘረው፣ በዝምታው የሚታወቀው የሰው ኃይል አስተዳደሩ ዳውድ፤ ‹‹እእህ…›› አለ፡፡ የቢሮ ኃላፊው ስለሚረዳው እንጂ የተናገረ ሳይሆን ሽንት ቤት ሆኖ፣ “ሰው አለ” ያለ ነበር የሚመስለው፡፡
‹‹የምትጨምረው ሀሳብ አለህ እንዴ ዳውድ?›› አለው የቢሮ ኃላፊው፡፡ ዳውድም ምንም የገጽታ ለውጥ በፊቱ ሳይታይ፤‹‹ያው አሁን በተነጋገርነው በሁሉም ነገር እስማማለሁ፤ እፈርማለሁም፡፡  ነገር ግን እርሷ ቀድማ የሥራ መልቀቂያ አስገብታለች›› አለ፡፡
     የቢሮ ኃላፊው መብረቅ የመታው ያክል ደርቆ ቀረ፡፡ ሌሎቹም ንስር እንደወሰዳት ጫጩት ነፍሳቸው ለሰከንዶች ቀጥ አለ፡፡ ሁሉም ክው አሉ፡፡ እንደገና ተያዩ፡፡ እስካሁን ስላልነገራቸው ተናደዱ፡፡ ነገር ግን የእሱን ባህርይ አብጠርጥረው ስለሚያውቁ ለምን እስካሁን አልነገርከንም በማለት ጊዜያቸውን ማጥፋት አልፈለጉም፡፡ ከዚህ በፊት ብዙ  ነገርን ታቅፎ ሳይነግራቸው  በመቅረቱ ተጨቃጭቀዋል፡፡ ብዙ ጥቅማ ጥቅምም ማግኘት እያለበት ትተውታል፡፡ አይታረምም እንጂ ማስጠንቀቂያ ደብዳቤም በተደጋጋሚ ተጽፎበታል፡፡ የሚገርመው ግን እስካሁን ማስጠንቀቂያ ደብዳቤዎቹ ምን እንደሚሉ አላነበባቸውም፡፡ የሚሰበሰበው ግዴታው ስለሆነ እንጂ ምንም ሳይናገር ስብሰባው የሚዘጋበት ጊዜ ብዙ ነው፡፡
‹‹እንዴት ሆኖ?›› አለ የቢሮ ኃላፊው፤ሁሉንም በአንዴ ለማየት እየሞከረ፤‹‹እኔ መጀመሪያም ያልኩት ይሄን ነው፡፡ ልትቀድመን አስባለች ማለት ነው›› አለ የግዢ አስተዳደሩ፡፡  
ሁሉም ሲደናገጡ ዳውድ ተረጋግቶ የሚሆነውን ይመለከታል፡፡ የሰው ኃይል አስተዳደር በመሆኑ ብዙ ነገሮች ይገጥሙታል፡፡ ነገር ግን ሁሉንም በንቀት ‹‹ከንቱ›› በማለት ያልፈዋል፡፡ በግዴለሽነት ብዙ ነገርን አሳልፏል፡፡ ምንም ይሁን ምን፣ ማንም ይሁን ማንም፣ ምንም አይመስለውም፡፡ ‹‹አይ አላህ ተው ሰውን ክፉ አታድርገው›› ይላል አንዳንድ ጊዜ ሲመረቅን፡፡ ሥራ ሆኖበት እንጂ ከጫት ውጪ ከማንም ጋር ባያወራ ደስታውን አይችለውም፡፡ ለመማርም ሆነ ራሱን ለማሻሻል እንደ ሌሎቹ አይሯሯጥም፡፡ የቢሮ ኃላፊው ብዙ ስለማይጨቀጭቀው ብቻም ሳይሆን ቢቆፍሩትም ምስጢር ባለማውጣቱ ይደነቅበታል፡፡ የማንንም ቢሆን ለማንም አያወራም፡፡ አንዳንድ ጊዜ ሲያጋንኑለት፤‹‹የሰማውን ወሬ ለሰው ሊያወራ ቀርቶ ለራሱም ደግሞ አይናገርም›› ይሉታል፡፡ በእርግጥም እሱ ካለበት ሳይነቃነቅ ብዙ ኃላፊዎች ተቀያይረዋል፡፡ ስላለፉትም ሆነ አሁን ስላሉት የሚናገረው ስማቸውን ብቻ ነው፡፡
ካልቀጠርከኝ ብለው ከሚጣሉት ሰዎች በተጨማሪ የበላይ ኃላፊዎችና ዳይሬክተሮቹ ዘመዳቸውን እያመጡ ቅጠርልን ስለሚሉት አንጀቱ ብግን፤ድብን ይላል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ይህን ሥራ ለቆ ለመሄድ ቢያስብም ሁሉም ቦታ ያው መሆኑን በመረዳቱ እየተጎዳ ይኖራል፡፡ ‹‹ሰው ክፉ›› ይላል  በዝምታው መሀል፡፡ መርቀን ብሎ ለሚወዳቸው እንደሚናገረው ከሆነ፣ ሁሉም መስሪያ ቤቶች በዚህ ጉዳይ አንድ ዓይነት ናቸው፡፡ አንዳንዱ በብሔር፣ አንዳንዱ በሀይማኖት፣ አንዳንዱ በጎሳ፣ አንዳንዱ በገንዘብ አለዚያም ጾታዊ ግንኙነት በማድረግ ቅጥር ይፈጸማል፡፡ ዳውድን የሚያናድደው ነገር ውድድር የሚባለው ከንቱ ልፋት ነው፡፡ ምንም እንኳን እሱም በሕጉ መሰረት ባይሰራም፣ ሁሌም ከራሱ ጋር እንደተካሰሰና እንደተዋቀሰ ይኖራል፡፡ ስንት የድሃ ልጅ እውቀቱን ተማምኖ፣ ስንት አገር አቋርጦ፣ ስንት ፍዳ ቀምሶ፣ ተቸግሮ፣ እየተራበ፣ ያልፍልኛል ብሎ እየተንከራተተ፣ ለይምሰል ማወዳደሩ በጣም ያናድደዋል፡፡ እንደውም ዳውድ በውድድር ጊዜ ከሩቅ አገር ያመለከቱትን አይደውልላቸውም፡፡ በዚህም የተነሳ ተወዳዳሪዎቹ በዳውድ ላይ አንዳንዴ ቂም ይይዙበታል፡፡ እርሱ ግን ውስጡን ስለሚያውቅ እንዳይንከራተቱ  በማሰብ ነው፡፡  ዳውድ በትክክል ያለፈውን ሰው ትቶ፣ የቢሮ ኃላፊው ቅጠር ያለውን የሚቀጥርበት ጊዜ አለ፡፡ እንደውም ቅጥር ከተፈጸመ በኋላ ‹‹ለፎርማሊቲው ማስታወቂያ አውጣ›› የሚባልበት ጊዜ በጣም ብዙ ነው፡፡ ‹‹አይ አላህ ኧረ ተው ሰውን ክፉ አታድርገው›› ብሎ የታዘዘውን እየተቃጠለ ይፈጽማል፡፡ ማንም ግን ንዴቱን አያውቅበትም፡፡ ከአፉ ክፉ ቃል መናገርም ሆነ  ሰው በእሱ እንዲከፋ አይፈልግም፡፡
‹‹ታድያ ምን እናድርግ?›› አለ የቢሮ ኃላፊው፤ጭንቀቱ እንዳይታወቅበት እየጣረ፡፡
የህዝብ ግንኙነቱ ዳይሬክተሩ ኤልያስም፤‹‹የሆነ ምክንያት ተፈልጎ መታሰር ነው ያለባት፡፡ አለዚያ ሌላ ችግር ውስጥ ታስገባናለች፡፡ በተለይ የባለፈው ጨረታ ከተመረመረ ብዙ ችግሮች ይገኙብናል፡፡ ሁላችንም ሸቤ መግባታችን ነው›› ሸቤ የምትለዋን ቃል ከተናገረ በኋላ ከአፉ ስላመለጠችው ተጸጸተ፡፡ ግን ማናቸውም ቢሆኑ አጽንኦት አልሰጧትም፡፡ አሊያም አልገባቸውም ወይንም ደግሞ ቀድመው ተረድተውት ይሆናል፡፡
‹‹እንዴት? ምን ዓይነት ምክንያት እንፈልግላታለን?›› አለ የፋይናንስ ኃላፊው ከጭንቁ የሚገላገልበት ዘዴ ያገኘ ስለመሰለው አንገቱን አስግጎ፡፡
የግዢ ኃላፊው፤‹‹በእርግጥ ከፈለግን ማስወንጀያ አናጣም፡፡ እርሷ ተወክላ የፈረመቺበት ሰነድ ይኖራል፡፡ በዚያ ልናሳሥራት እንችላለን›› አለ፡፡
የፋይናንስ አስተዳደሩ እንደ መሳቅም እንደ መናደድም ብሎ፤ ‹‹እኔስ? ታዝዤ ነው የፈረምሁት ልበል? ወይስ ተሳስቼ ነው እንድል ትፈልጋለህ? ማንም ይፈርመው አግባብ ከሌለውና ችግር ካለበት እንደ ፋይናንስ አስተዳደርነቴ የማስቆም ኃላፊነት አለብኝ፡፡ እሱ ሌላ መዘዝ ነው፡፡ ሌላ መፍትሔ ካለህ ተናገር›› አለ በማያወላውል አቋም፡፡  
በሆነ ጊዜ የቢሮ ኃላፊው እየወከላት ብዙ ጊዜ ይጠፋ ነበር፡፡ በርከት ያለች ብር ከሆነች ስብሰባ፣ ስልጠና፣ መስክ እያለ በምክንያት  ወክሏት ይሰወር ነበር፡፡ ያኔም በስልክ ፈርሚላቸው ብሏት በስንት ጭቅጭቅ አሳምነዋት የፈረመቺው ሰነድ ስለነበር በዚያ ለመወንጀል ፈልገው ነበር፡፡ ያም ቢሆን እንዳማያዋጣቸው ተረድተዋል፡፡ ኤፍራታ መርዝ ስለሆነች መረጃ ይዛባቸው እንደሆነም ይጠራጠራሉ፡፡                  
የግዢ ኃላፊ፤‹‹ሌላ አማራጭ… አ…ለ! ለምን እንዳትሞት አድርገን በመኪና አናስገጫትም፡፡ ከዚያ እናሳክማታለን፣ እንከባከባታለን›› አለ፡፡
የሰው ኃይል አስተዳደሩ ዳውድ በድንገት፤‹‹ያረሱል አሚን ያለህ! ኧረ በጭራሽ ይህ የማይሆን ነው›› አለ፡፡ እንደ ዳውድ ሌሎቹም አይቃወሙ እንጂ ሁሉም ደግንጠዋል፡፡ ምክንያቱም እንደ እነሱ በሙስና አልጨማለቅም ማለቷ እንጂ ባህሪይዋን፣ መልካምነቷን፣ በሥራዋ ያላትን ታማኝነትና ጥንካሬ፣ ከሁሉም በላይ ለአመነችበት ነገር ያላትን ጽናትና ክብር የቢሮ ኃላፊው ጭምር ያደንቁላታል፡፡ ይወዱላታልም፡፡ ምን ይደረግ? ወይ አትበላ ወይ አታስበላ!   
     ‹‹እና ምን ይሁን? እንደማይመለከትህ እጅህን አጣጥፈህ ዝም ትላለህ እንዴ? አደጋ ውስጥ እንዳለን ታውቃለህ አይደል? ከርቸሌ ከገባን ሁላችንም እንደምንገባ እወቁ፡፡ የምንፈራረማቸው ቃለ-ጉባዔዎች እስካልተፈተሹ ጊዜ ድረስ ነው ህጋዊ ሆነው የሚቀጥሉት፡፡ ከተመረመሩ ግን…›› አለው በእሷ ቦታ የተወከለው ምክትል ቢሮ ኃላፊው ዳውድን በቁጣ፡፡ በእሷ ቦታ የተወከለው አስመሳይና ተሽቆጥቋጭ ስለሆነ ነው እየተባለ ይታማል፡፡ ‹
‹ማንን ታሸንፋለህ ሲባል፣ ወደ ሚስቱ ሮጠ›› እንዲሉ አበው መሆኑ ነው፣ ዳውድ ላይ መጮሁ፡፡ ይህቺ ሹመት ከተሰጠችው በኋላ ተራ ሰራተኞችን ማናገር እያንገሸገሸው ነው፡፡የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተሩ ኤልያስ፤‹‹ለምን እንዲህ አናደርግም፡፡ ሙስና አልበላም እያለች አይደል የምትመጻደቀው፣ የእኛ መዝገብ ቤቷ ልጅ ብድር አለብኝ ስትል ሰምቻለሁ፡፡ እዳሽን ክፈይ ብለን ልከናት ፎቶ እናነሳታለን፡፡ ከዚያም ፖሊሰ አሰማርተን ሙስና እየተቀበለች ነው ብለን ማሳሰር ነው፡፡ የመዝገብ ቤቷ ልጅ የተወሰነ ብር ከሰጠናት ለፍርድ ቤት ቃሏን እስከ መስጠት ትተባበረናለች፡፡ ምስክር ካስፈለገም ጓደኛዋን በገንዘብም፣በፍቅርም መቅረብ እንችላለን፡፡
ደመወዝ እንደሚጨመርለትና እድገት እንደሚሰጠው ተነግሮት፣በዚህ ኑሮ ውድነት እምቢ የሚል ሰራተኛ አይኖርም›› አለ ከሌሎቹ የተሻለ ብልህ ነኝ ብሎ ስለሚያስብ ዓይነ ዓይናቸውን እያየ፡፡ ሁሉም በየተራ  መፍትሄ የሚሉትን ሀሳብ አቀረቡ፡፡ በጸጥታ ሲከታተል የነበረው የቢሮ ኃላፊው ተናደደ፡፡ የአንዳቸውም ሃሳብ አላረካውም፡፡ ጉዳዩን ላያዳግም መቅበር ነው ፍላጎቱ፡፡ ‹‹ስንት አስቸጋሪና ውስብስብ ነገር እንዳላለፍን አንዲት እንከፍ ታስቸግረን!? በሽጉጥ  ነበር መድፋት፡፡ ብይ! ተጠቀሚ፣ ከሰው እኩል ሁኚ ስትባል እንቢ ትላለች? እሷ ብሎ የአገር ተቆርቋሪ፡፡ እንኳን እሷ ስንቶቹ የአገሪቱ ከፍተኛ ባለሥልጣንም ይመዘብራሉ፡፡
አዲስ ነገር ነው እንዴ? ቆይ አሳያታለሁ›› አለ ጠረጴዛውን በመደብደብ፡፡ ሲናደድ ግንባሩ ከመቆጣጠሩና ላቡ ግጥም ከማለቱ በላይ ዓይኑ በክፋት የተሞላች የተኩላ ዓይን ትመስላለች፡፡
     የቢሮ ኃላፊው፤‹‹በቃ ሁሉንም ለኔ ተውት›› ብሎ የስልኩን እጀታ አነሳ፡፡ ‹‹ዳውድ እቤቷ ወስደህ የምታስቀምጥልኝ ነገር አለ፡፡ ኤልያስ የባለፈውን ሰነድ እንድታመጣልኝ፡፡ አንተ ደግሞ ሰሞኑን ከእሷ ጋር ስለሚውለው ሰው ማንነት ሙሉ መረጃ እንድትነግረኝ እፈልጋለሁ፡፡
አንተኛው ፋይሎቹን በሙሉ ‹‹ኮፒ›› አድርግና በተነጋገርነው መሰረት እንደገና ሥራቸው፡፡ ሁላችሁም ተዘጋጁ፤የምነግራችሁንና የማዛችሁን ሰከንድ ሳታባክኑ፣ ሳትጠራጠሩ ማድረግ ነው፡፡ ምንም አታስቡ፤ስልጣኔን በአግባቡ የምጠቀምበት ሰዓት ይህ ነው›› አለ፡፡  ከዚያም በውል ወደሚያውቁት የደህንነት ሰው ጋ ስልክ ደውሎ፤ ስለ አክራሪነት፣ ሽብርተኝነትና ልማት አደናቃፊዎች ጥቂት ካወራ በኋላ በቢሮአቸው ውስጥ ስለተከሰተው ነገር ተገናኝተው ዝርዝሩን ማውራት እንዳለባቸው ተነጋግሮ ስልኩን ዘጋ፡፡ ሁሉም ተደናገጡ፡፡ አብዛኛዎቹ ነገሩ ወደ ሌላ እየተቀየረ መሆኑ ገባቸው፡፡
እውነትም እጀ ረጂም!! ‹‹እኔ የማደርገውን አሳያችኋለሁ፡፡ እድሜ ልኳን ትበሰብሳታለች፡፡
ሁላችሁም ለተልእኮው ተዘጋጁ፡፡ አንተ እንከፍ ደግሞ ስልክህን እንዳታጠፋ›› ብሎ  ምክትል ቢሮ ኃላፊውን ገላምጦት፣ ከእጁ የማትለየውን ጥቁር ቦርሳ አንጠልጥሎ ጥሎአቸው ወጣ፡፡ ሁሉም  ቆሌያቸው ተገፎ በዓይናቸው ሸኙት፡፡ ማንም ምንም ያለ አልነበረም፡፡ ጉዳዩ ከባድና የሁላቸውም እጅ እንደሚኖርበት ተገንዝበዋል፡፡ የቢሮ ኃላፊው ሁሉንም በማነካካት ለዘላለም በደም ተሳስረው እንዲኖሩ ማድረግን ያውቅበታል፡፡
 ማንም ከደሙ ንጹህ ነኝ ማለት አይችልም፡፡ ወደ ኋላ የሚያፈገግፍ ቢኖር የእሷ እጣ ፋንታ እንደሚደርስበትም አላጡትም፡፡ ዳውድ እንደ መሳቅ ብሎ የመጀመሪያው መልእክተኛ በመሆኑ እየተገረመ፤‹‹አሁን ከእኛ በላይ ልማት አደናቃፊ አለ!›› ሲል በምጸት ተናገረ፡፡
ከእርሱ በቀር ሁሉም ደንግጠው ስለነበረ የመለሰለት አልነበረም፡፡ ግዴለሽነቱ ከጭንቀት ቢያድነውም፣ከዚህ መ/ቤት በጊዜ ባለመልቀቁ መቆጨቱ አልቀረም፡፡
ሁሉም በየራሳቸው ዓለም በተቀመጡበት በሀሳብ ሰመጡ፡፡ “ዋ! ለኔ ….. ዋ! ለኔ…” የሚሉ ነፍሶች ተበራከቱ፡፡ ዳውድ ግን አሁን ወንድ መሆን እንዳለበት፤እንደተጫወቱበት የሚጫወትባቸው ጊዜ እንደደረሰ አሰበ፡፡ ‹‹ተጀመረ…!›› አለና በንቀት አይቷቸው፣እሱም ከቢሮው ወጣ፡፡ በድርቅ የተመታው የቢሮአቸው የፍትህ ኤልኒኖ፣ መከላከያው በእጆቹ ውስጥ ባሉት ዶሴዎች እንደሆነ እርግጠኛ ነበር፡፡  





    በአመልማል ደምሰው የተደረሰውና በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተው “ያልተቋጨ ጉዞ” የተሰኘ ልብ ወለድ መፅሀፍ የፊታችን አርብ ከቀኑ 11፡30 ሰዓት ጀምሮ በዋቢ ሸበሌ ሆቴል ይመረቃል፡፡ መቼቱን ጎንደር፣ ኤርትራ (አስመራ) አዲስ አበባ፣ ጅማና አሜሪካ ያደረገው ልብወለዱ፤ ልጅነትና ፍቅር ያላቸው ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ትስስር በውብ ቋንቋ ተገልፆበታል ተብሏል፡ ፡ በምርቃት ስነ - ስርዓቱ ላይ ደራሲያንና ገጣሚያን ስራዎቻቸውን እንደሚያቀርቡም ታውቋል፡፡ በ387 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ በ80 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

    ወደ እስራኤል አገር ለስራ ተጉዛ በመኖሪያ ፈቃድ እጦት ለእስር በተዳረገችው አብነት ከበደ የተፃፉ ወጐችና ግጥሞችን ያካተተው “በኖት በህደሪም” የተሰኘው መድበል ሰሞኑን ገበያ ላይ ዋለ፡፡ ፀሐፊዋ በእስራኤል አገር የመኖሪያ ፈቃድ ሳትይዝ በመገኘቷ ከመንገድ ላይ ተይዛ ከርቸሌ የተወረወረች ሲሆን በሁለት ዓመታት የእስር ቆይታዋ ያሳለፈችውን መከራ በወቅቱ ከእነስሜቷ በሁለት ወጐችና በበርካታ ግጥሞች ከትባዋለች ተብሏል፡፡ መጽሐፉ ባለፈው ሳምንት የተመረቀ ሲሆን በ45 ብር እንደሚሸጥ ታውቋል፡፡