Administrator

Administrator

Saturday, 11 June 2016 12:36

ፀሐፍት ጥግ

(ስለ እናት አገር)
- እናት አገር ላይ ክህደት ለፈፀሙ በሰዎች
የተፃፉ መፃህፍትን አላነብም፡፡
ቭላድሚር ፑቲን
- እኔ የምፈልገው ወደ እናት አገሬ ባንግላዲሽ
ወይም ወደ ጉዲፈቻ አገሬ ህንድ መመለስ
ነው፡፡
ታስሊማ ናስሪን
- ለጀግና ሰው፤ ዓለም በሙሉ እናት አገሩ
ናት፡፡
አቪድ
- ለሰው ልጅ እውነተኛ ፍቅር የሌለው፤
ለእናት አገር እውነተኛ ፍቅር አይኖረውም፡፡
አናቶሌ ፍራንስ
- የእናት አገርህ ዜጋ ብትሆንም ሁሉንም
አገራትና ሁሉንም ሃይማኖቶች በእኩል
አክብር፡፡
ሳዝያ ባባ
- በእናት አገርህ ክብር ይሰማህ፡፡ እናትህ
እንደወለደችህ ሁሉ እናት አገርህም
ወልዳሃለች፡፡
ሳዝያ ባባ
- አገር ወዳድነት ግሩም ነገር ነው፡፡ ግን
ለምንድን ነው ፍቅር በድንበር ላይ
የሚቆመው?
ፓብሎ ካሳልስ
- የአገር ፍቅር በማይረቡ ምክንያቶች
ለመግደልና ለመገደል ፈቃደኛ ነው፡፡
በርትራንድ ራስል
- ሰዎች አገራቸውን የሚወዱት ታላቅ
ስለሆነች አይደለም፤ የራሳቸው ስለሆነች
እንጂ፡፡
ሴኔካ
- የሰው አገሩ የተወሰነ መሬት፣ ተራሮች፣
ወንዞችና ደኖች አይደሉም፤ ይልቁንም
መርህ ነው፤ አገር ወዳድነት (አርበኝነት)
ለዚያ መርህ ታማኝ መሆን ነው፡፡
ጆርጅ ዊሊያም ኩርቲስ
- የአቴንስ ወይም የግሪክ ተወላጅ
አይደለሁም፤ እኔ የዓለም ዜጋ ነኝ፡፡
ሶቅራጠስ
- አገር ወዳድነት የሃይማኖት ዓይነት ነው፤
ጦርነቶች የሚፈለፈሉበት እንቁላል ነው፡፡
ጊዴ ሞፓሳ

Saturday, 11 June 2016 12:27

የዘላለም ጥግ

በራስ ስለመተማመን)
- በራስ መተማመን ከሌለህ በህይወት ውድድር
ሁለቴ ተረተሃል፡፡
ማርከስ ጋርቬይ
- እውነቱን ለመናገር የሰዎች በራስ መተማመን
ከገንዘብ የበለጠ ዋጋ አለው፡፡
ካርተር ጂ.ውድሰን
- የ4 ዓመት ልጅ ሳለሁ ወንድምና እህቶቼ
በረሃብ አለቁ፡፡ እናም ስኬትን የተቀዳጀሁት
በልበ ሙሉነት፣ ራስን በማነሳሳትና ተግቶ
በመስራት ነው፡፡
ቼን ጊዋንግብያኦ
- ተሰጥኦን ልታስተምር አትችልም፡፡
እግዚአብሔር ያጎደለውን አንተ አትሞላውም።
በራስ መተማመንን ግን ልታስተምር
ትችላለህ፡፡
ግሎርያ ናይለር
- በራስህ ተማመን፡፡ የሰው ልጅ እጅግ ማራኪው
ክፍል በራስ መተማመን ይመስለኛል፡፡
ኩርቲስ ጃክሰን
- በራስ መተማመን የሚመነጨው ከሰዓታት፣
ከቀናት፣ ከሳምንታትና ከዓመታት የማያቋርጥ
ሥራና ታታሪነት ነው፡፡
ሮጀር ስታውባች
- ህዝቦች በመሪዎች ላይ ያላቸው እምነት፣
መሪዎች በህዝቦች ላይ ያላቸውን ልበ ሙሉነት
ያንፀባርቃል፡፡
ፓውሎ ፍሬይሬ
- ውበት ብዙ መልኮች አሉት፡፡ እጅግ ውቡ
ነገር በራስ መተማመንና ራስህን ማፍቀር
ይመስለኛል፡፡
ኪስዛ
- በራስ መተማመን ካለህ ከመጀመርህ በፊት
ድል አድርገሃል፡፡
ማርከስ ጋርቬይ
- በራስ መተማመን የሚመጣው ከብስለት ጋር
ነው፤ ራስን ይበልጥ በመቀበል፡፡
ኒኮሎ ሼርዚንገር
- ሳንሱር፤ የህብረተሰብን በራስ የመተማመን
ስሜት ማጣት ያንፀባርቃል፡፡
ፖተር ስቲዋርት
- በራስ መተማመን የሚመነጨው ከዲሲፕሊንና
ከልምምድ ነው፡፡
ሮበርት ኪዩሳኪ
- ሁልጊዜ አንባቢዎቼ በእኔ ላይ በሚያሳድሩት
ልበ ሙሉነት እደነቃለሁ፡፡
ሜሪ ካር


5 ቢሊዮን ብር ተመድቧል
     የመምህራንን ደሞዝ ለማሻሻል በመንግስት የተመደበው የ5 ቢሊዮን ብር በጀት፣ የመምህራኑን ደሞዝ በእጥፍ ሊያሳድግ የሚችል ከፍተኛ ጭማሪ ነው፡፡ ለአስተማሪዎች “ትርጉም ያለው የደሞዝ ጭማሪ ይደረጋል” በማለት መንግስት በደፈናው መግለጫ ቢሰጥም፤ እስካሁን ዝርዝር መረጃ አላቀረበም፡፡ ጭማሪውም በዝርዝር ተሰልቶ ለትምህርት ተቋማት ገና አልተደላደለም፡፡
የዛሬ ሁለት ዓመት፣ ለመንግስት ሰራተኞች ደሞዝ ለመጨመር ውሳኔ ተላልፎ፣ ልዩ በጀት ተመድቦ እንደነበር የሚታወስ ሲሆን፣ ዘንድሮም በተመሳሳይ ሁኔታ ለመምህራን የደሞዝ ማሻሻያ፣ የ5 ቢ. ብር ልዩ በጀት ተመድቧል፡፡ ያኔ ለሁሉም የመንግስት ሰራተኞች፣ ለደሞዝ ማሻሻያ ተብሎ የተመደበው ልዩ በጀት 7 ቢ ብር እንደነበር የሚታወስ ሲሆን፣ በአማካይ የሰላሳ በመቶ የደሞዝ ጭማሪ ለማድረግ ውሏል፡፡
ከዚህ ጋር ሲነፃፀር ዘንድሮ ለመምህራን ብቻ የተመደበው የደሞዝ ጭማሪ በጀት 5 ቢሊዮን ብር መሆኑ ጭማሪው ከፍተኛ እንደሚሆን ያሳያል፡፡ የአገሪቱ የመምህራን ብዛት ሩብ ሚሊዮን እንደሚሆን የሚገመት ሲሆን፣ የወር ደሞዝ ጭማሪው በአማካይ 2500 ብር ገደማ ነው፡፡ ይህም የመምህራንን ደሞዝ በእጥፍ ለማሳደግ ያስችላል፡፡

• “በአመት 1 ቢ.ዶላር የውጭ ምንዛሬ ያስገኛል”
• ግድቡ የአፄ ኃይለስላሴ ህልም ነበረ - ታይም መጽሔት

ህዳሴ ግድብ ከአመት በኋላ ኤሌክትሪክ ማመንጨት እንደሚጀምር የዘገበው ታይም መጽሔት፣ ግንባታው፣ ከ4 ቢሊዮን ዶላር በላይ የሚፈጅ ቢሆንም፣ በየዓመቱ 1. ቢ ዶላር ገቢ ሊያስገኝ እንደሚችል ገለፀ፡፡
የአገሪቱ የኤሌክትሪክ አቅርቦት፣ የህዳሴ ግድብ ሲጨመርበት፣ አራት እጥፍ እንደሚሆን መጽሔቱ ጠቅሶ፤ የአገር ውስጥን የኤሌክትሪክ እጥረት ያቃልላል፤ ከሱዳንና ከግብጽ ማሰራጫ መስመሮች ጋር ሲገናኝም፣ በየዓመቱ 1 ቢ.ዶላር የውጭ ምንዛሬ እንደሚያስገኝ የኤምአይቲ ጥናት ያሳያል ብሏል፡፡
አፄ ኃይለስላሴ፣ ግድቡን የመገንባት ህልም እንደነበራቸውና የዛሬ ሃምሳ ዓመት ግንባታውን ለማካሄድ ወስነው እንደነበር አስታውሷል - መጽሔቱ፡፡ የገንዘብ እጥረት፤ የፖለቲካ አለመረጋጋት፣ ከባድ የድርቅ አደጋ፣ የደርግ መፈንቅለ መንግስት…ሌሎችም በርካታ ችግሮች ተደራርበው፣ የግድቡ ዕቅድ ለግማሽ ምዕተዓመት ዘግይቷል፡፡
በ2003 ዓ.ም በጠ/ሚ መለስ ዜናዊ ይፋ የተደረገው የግድብ ግንባታ፣ አሁን እንደተጋመሰና በግዙፍነቱ በአፍሪካ ቀዳሚ እንደሆነ መጽሔቱ ጠቅሶ፤ በግድቡ የሚፈጠረው ሃይቅ የወንዙን ውሃ ሙሉ ለሙሉ የማጠራቀም አቅም አለው ብሏል። በሚቀጥለው አመት ኤሌክትሪክ ማመንጨት እንደሚጀምርም መጽሔቱ በሰሞኑ እትሙ ገልጿል።

በግንባታ ስራ ላይ መሰማራት ሳያዋጣ አይቀርም፡፡ ከፌደራል በጀት ውስጥ 75 ቢ. ብር ለግንባታ የተመደበ ነው፡፡
በትልቅ በጀት ቀዳሚነቱን የያዘው፣ የመንገድ ግንባታና ጥገና ነው - 46 ቢ. ብር፡፡
38 ቢ. ብር የተመደበላቸው ዩኒቨርስቲዎች፣ ሁለተኛ ደረጀ ላይ ተቀምጠዋል - በገንዘብ ብክነትና በዝርክርክነት ግን አንደኛ ሆነዋል፡፡
26 ቢ. ብር - መጠባበቂያ እህል ለማከማቸት ይውላል ተብሏል፡፡
14 ቢ. ብር ለእዳ ክፍያ (10 ቢ. ብሩ ለወለድ ክፍያ ነው)
11 ቢ. ብር ለመከላከያ፣ 2.3 ቢ. ብር ለፌደራል ፖሊስ፣ 1.2 ቢ. ብር ለብሔራዊና ለመረጃ ደህንነት
የእርሻ በጀት 8.6 ቢ ብር ቢሆንም፣ እንደ ድሮው ለምርት እድገት ሳይሆን፣ በአብዛኛው ለችግረኞች ድጐማ ተመድቧል፡፡
8.8 ቢ. ብር ለውሃ የተመደበ ነው፡፡ ግን በሃብት ብክነቱም ቀላል አይደለም፡፡ ከአስር ዓመት በፊት ይጠናቀቃሉ የተባሉ፣ ግድቦች ዘንድሮም ብዙ መቶ ሚሊዮን ብር ተመድቦላቸዋል
ለጤና አገልግሎት የሚውለው ገንዘብ 8.2 ቢሊዮን ይሆናል፡፡ ከዚህ ውስጥ 6 ቢ. ብር በውጭ አገር እርዳታ የሚሸፈን ነው - በአብዛኛውም በአሜሪካ መንግስት እርዳታ፡፡
በሚቀጥሉት ሁለት ሳምንታት በፓርላማ ይፀድቃል ተብሎ የሚጠቀበቀው የ274 ቢሊዮን ብር በጀት፣ በአገሪቱ ኢኮኖሚ ውስጥ የመንግስት ድርሻ እየገዘፈ መምጣቱን የሚያሳይ ሲሆን፣ የእቅድ ትኩረቶችንና ስራዎችን ይዘረዝራል፤ የሃብት ብክነት አደጋዎችንም ይጠቁማል፡፡ ፌደራል መንግስት ከሚያንቀሳቅሰው ሃብት ውስጥ 40% ያህሉ ለግንባታ የሚውል በመሆኑ፤ የመንግስት የእቅድ ትኩረት፣ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ፣ ሰራተኞችና ኢንቨስተሮች በግንባታ መስክ እንዲሰማሩ የሚገፋፉ ነው ብሎ መናገር ይቻላል፡፡ በሌላ በኩልም፤ በሃብት ብክነት ኦዲተርን ያማረሩ  ዩኒቨርሲቲዎች፣ ብዙ ገንዘብ የሚመደብላቸው ተቋማት ስለሆኑ፣ የብክነትና የሙስና አደጋው ከፍተኛ እንደሆነ ያመላክታል - በጀቱ፡፡
በእርግጥ፣ ትልቅ በጀት ከተመደበ፣ ብዙ ሃብት ይባክናል ማለት አይደለም፡፡ ከሌሎች ስራዎች ጋር ሲነፃፀር፣ ለመንገድ ግንባታ የሚውለው ሃብት በአመዛኙ ውጤታማ ነው ማለት ይቻላል፡፡ በበጀት ትልቅነት ደግሞ የመንገድ ግንባታን የሚስተካከል የለም - 46 ቢ. ብር ነው የተመደበለት፡፡ በዚህ መስክ ብዙ ብክነት የማይታየውና የአገሪቱ የአስፋልት መንገድ የተሻሻለው አለምክንያት አይደለም፡፡
ከንጉሱ ዘመን ጀምሮ፤ የመንገድ ግንባታ በደህና ሙያዊ መሰረት ላይ መዋቀሩ፣ እንዲሁም ዋና ዋናዎቹ የመንገድ ግንባታዎች በአለማቀፍ የጨረታ አሰራር ለተለያዩ ኩባንያዎች በኮንትራት የሚሰጡ መሆናቸው፤ ለውጤታማነቱ አስተዋጽኦ አበርክተዋል፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በፌደራልና በክልል ደረጃ፣ መንግስታዊ ድርጅቶች ወደ መንገድ ግንባታ እንዲገቡ መደረጋቸው ግን፣ ለወደፊት አሳሳቢ መሆኑ አይቀርም። የሃብት ብክነትን ያስከትላሉ፡፡ በፌደራልና በክልል መንግስታዊ ድርጅቶች አማካኝነት ላለፉት 12 ዓመታት ሲካሄዱ የቆዩ የግድብ እና የመስኖ ፕሮጀክቶችም፣ አደጋውን አጉልተው ያሳያሉ፡፡
ባለፉት ዓመታት፤ በርካታ ቢሊዮን ብር የፈሰሰባቸው የተንዳሆ፣ ከሰምና የረብ የመስኖ ግድብ ፕሮጀክቶች፣ የዛሬ አስር ዓመት እንዲጠናቀቁ ነበር የታሰበው፡፡ ነገር ግን ዘንድሮም 500 ሚሊዮን ብር ተመድቦላቸዋል፡፡
ለአስር ዓመት በተጓተቱት ስራዎች ብዙ ቢሊዮን ብር ሃብት ባክኗል፡፡
ነገር ግን በሃብት ብክነትና በዝርክርክ አሰራር፣ ዩኒቨርሲቲዎችን የሚፎካከር አልተገኘም፡፡ ከአመት አመት የዩኒቨርስቲዎቹ አሰራር ከመስተካከል ይልቅ እየተባባሰ በመምጣቱ የተማረሩት የፌደራል ዋና ኦዲተር፤ ዩኒቨርሲቲዎቹ በቀጥታ ሃብት እንዳያንቀሳቅሱ መከልከልና፣… በተለይ የእቃ ገዢዎችን በበላይነት የሚመራ ሌላ ተቋም መፍጠር እንደሚያስፈልግ ገልፀዋል፡፡
ኦዲተርን ያማረሩት 34 ዩኒቨርስቲዎች ናቸው - በዓመት ውስጥ 38 ቢሊዮን ብር የሚመደብላቸው። የሃብት ብክነቱና የሙስና አደጋውም የዚያኑ ያህል ከፍተኛ እንደሚሆን፣ የዋና ኦዲተሩ ተደጋጋሚ ሪፖርት ይመሰክራል፡፡
የመጠባበቂያ እህል ለማከማቸት የተመደበው የ26 ቢሊዮን ብር በጀት፣ በሦስተኛ ደረጃ የሚጠቀስ ሲሆን፤ ከዚህ ቀጥሎ ከፍተኛ ድርሻ የወሰደው የብድር ክፍያ ነው፡፡ መንግስት ብድር ለመክፈል ከሚያውለው 14 ቢሊዮን ብር ውስጥ፣ 10 ቢ. ብር ያህሉ የብድር ወለድ ነው፡፡ እንዲህም ሆኖ በመንግስት በጀት ውስጥ የማይካተቱ ሌሎች ከባድ ብድሮች አሉ፡- የቴሌ፣ የስኳር ፕሮጀክቶች፣ የኤልፓ፡፡ እነዚህ ሲጨመሩበት፣ መንግስት የውጭ ብድር ለመክፈል በዓመት ከሃያ ቢሊዮን ብር በላይ ያወጣል፡፡
ነገር ግን፣ አሁንም የበጀት ጉድለት ለመሙላትና የተለያዩ ፕሮጀክቶችን ለማከናወን፣ ተጨማሪ ብድር መከማቸቱ አይቀርም፡፡ በተለይ ውጤታማ ያልሆኑ ፕሮጀክቶችና ምርታማነትን የማያሳድጉ ዕቅዶችን ለማስፈፀም የሚመጡ ብድሮች ለወደፊት አደጋ ናቸው፡፡ ከአስር ዓመት በፊት አብዛኛው የእርሻ በጀት፣ ለምርጥ ዘር ምርምር፣ ለቴክኒክ ስልጠና፣ ለማዳበሪያና ለመሳሰሉ ጉዳዮች ነበር የሚመደበው - ምርታማነትን ያሳድጋሉ በሚል፡፡ ከዚያ ወዲህ ግን ችግረኛ ገበሬዎችን ለመደጐም የሚውለው የእርሻ በጀት እየገነነ መጥቷል። ነገር ግን፣ ድጐማ የሚደረግላቸው ገበሬዎች፤ ወደ ምርታማነት ሲያድጉ አይታይም፡፡ እናም ድጐማው እየተስፋፋ ዘንድሮ 6 ቢሊዮን ብር ደርሷል - ከጠቅላላው 8.2 ቢ. ብር የእርሻ በጀት፡፡

    በዩኔስኮ የዓለም አስደናቂ ቅርሶች ከተመዘገቡትና የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት አካል የኾኑት የቤተ ሩፋኤልና ቤተ ገብርኤል አብያተ መቅደሶች፤ በረጅም ጊዜ አገልግሎትና በተፈጥሮ በደረሰባቸው የመሠንጠቅና የማፍሰስ ጉዳት የተነሣ በከፍተኛ አደጋ ውስጥ የነበሩ ሲኾን፤ በ15 ሚሊዮን ብር ወጪ ውጤታማ ጥገና እንደተደረገላቸው ተገለጸ፡፡
ከዩኔስኮ፣ ከዓለም ቅርስ ፈንድ(World Monument Fund) እና ከአሜሪካ መንግሥት(American Ambassador’s Fund) በተገኘው የገንዘብ ድጋፍ የተካሔደውን የጥገና ፕሮጀክት በሓላፊነት ያሠራው በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን ነው፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የቅርስ ጥበቃ መምሪያም፤ ከፕሮጀክቱ ጥናት እስከ ፍጻሜው ድረስ ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ በባለቤትነት መሳተፏ ታውቋል፡፡
አምስት ዓመት በወሰደው የፕሮጀክቱ ጥናት መሠረት፣ ኦልሚ ኦሊንዶ የተባለ አገር በቀል ደረጃ አንድ ኮንትራክተር የአብያተ መቅደሶቹን ጥገና ባለፉት ዘጠኝ ወራት ሲያካሔድ የቆየ ሲኾን፤ የፌደራል ሳይንቲፊክ ኮሚቴ ያስተባበራቸው ኢትዮጵያውያን አርክቴክቸሮችና ጂኦሎጂስቶች ከታዋቂ የእንግሊዝና የጣሊያን ባለሞያዎች ጋር መሳተፋቸው ተጠቅሷል፡፡
የውቅር አብያተ ክርስቲያናቱን አካባቢ የኅብረተሰብ ክፍሎች ያቀፈ ኮሚቴም ለፕሮጀክቱ መሳካት የበኩላቸውን ድርሻ እንደተወጡና፤ የደብሩ አስተዳደርና ማኅበረ ካህናት ጸሎትም እገዛ እንዳደረገ፣ ባለፈው ሳምንት እሑድ የፕሮጀክቱን መጠናቀቅ አስመልክቶ በስፍራው በተካሔደ የምረቃ መርሐ ግብር ላይ ተገልጿል፡፡
በዓለም ቅርስነት የሰፈሩት የደብረ ሮሃ ቅዱስ ላሊበላ አብያተ ክርስቲያናት፣ ከ800 ዓመት በላይ ዕድሜ ያስቆጠሩና ከአንድ ወጥ አለት ተፈልፍለው የተሠሩ 11 ውቅር አብያተ መቅደሶች ያሉት ሲኾን፣ የቱሪስት ፍሰቱን ያጠናክራል የተባለ አስጎብኚ ቢሮ በአዲስ አበባ ለመክፈትና ሕንፃ ለማስገንባት የደብሩ አስተዳደር መዘጋጀቱ ተጠቁሟል፡፡
በተያያዘ ዜና፣ የአብያተ መቅደሶቹን ጥገና በቴክኒክና በገንዘብ የደገፈው የዓለም ቅርስ ፈንድ፣ በተመሳሳይ ጉዳት ላይ ለሚገኘው የይምርሐ ክርስቶስ ቤተ መቅደስ የቅድመ ጥገና ጥናት፤ 150 ሺሕ ዶላር መለገሡንና የጥናት ስምምነቱም፣ በፈንዱ የአፍሪካ ጉዳዮች ዋና ዳይሬክተርና በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር መካከል ከኹለት ወራት በፊት መፈረሙ ተገልጿል፡፡

      ሰው በሀገር ይወለዳል ይባላል። ግን ደግሞ ሀገርን የሚወልዱ ሰዎች አሉ።  
አብደላ እዝራ ጥበብና ፍቅር የተቃቀፉበት ሀገር በውስጡ ተሸክሟል።አብሮም ኖሯል።  የምናውቀው በተባ ብዕሩ፣በሰላ ሂሱ፣ስለ ጥበብ ሲል ሁሉንም በሚተው ኪናዊ ፍቅሩ ነው።  የአንጋፋ ደራስያንን ሥራ ፈትኗል፤የረገበውን የሀገር ጥበብ ቆንጠጥ አድርጎ በከፍታ አጉልቶ ለማሳየት።  ጠቢባን የሚያደንቁ ውብ ዓረፍተ ነገሮችን ዘክሯል። እምቡጥ አበቦቹን ወጣት ደራሲያንን በሚሳሳ እጁ ኮትኩቷል።  ቸርነቱ በጥበብም በቁስም ነው።   አብደላ እዝራ ጭው ባለ በረሃ ውስጥ ዕድሜውን ሙሉ ለጥበብ ንጽህና እንደ ምንጭ
የፈሰሰ ጅረት ነበር!   በፈረሰው  ቅጥር -----     የቆመ የጥበብ ዘብ!!
                                   *********   
        አንጋፋው የጥበብ ሃያሲና የአዲስ አድማስ ጸሐፊ እዝራ አብደላ፣ ቅዳሜ ግንቦት 28  ቀን 2008  ከዚህ ዓለም በሞት  ተለይቶናል። የቀብር ሥርዓቱ እሁድ ተፈጽሟል።  ለቤተሰቡ፣ለወዳጆቹ፣ለአድናቂዎቹና ለጥበብ አፍቃሪያን መጽናናትን እንመኛለን።


ከጥር ወዲህ ከ2 ሺህ 500 በላይ ሰዎች ለሞት ተዳርገዋል

አለማቀፉ የስደተኞች ተቋም በዚህ ሳምንት በሜዲትራኒያን ባህር ላይ ስደተኞችን አሳፍረው
ሲጓዙ በነበሩ ጀልባዎች ላይ በደረሱ አደጋዎች  አለማቀፉ የስደተኞች ተቋም በዚህ ሳምንት በሜዲትራኒያን ባህር ላይ ስደተኞችን አሳፍረው ሲጓዙ በነበሩ ጀልባዎች ላይ በደረሱ አደጋዎች ለሞት የተዳረጉ የተለያዩ አገራት ዜጎች ቁጥር 1 ሺህ ያህል እንደደረሰ ማስታወቁን ዘ ጋርዲያን ዘገበ፡፡ካለፈው ጥር አንስቶ በሜዲትራኒያን ባህር በደረሱ የጀልባ አደጋዎች ከ2 ሺህ 500 በላይ ስደተኞች ህይወታቸው እንዳለፈ የገለጸው ተቋሙ፤ በአካባቢው በሚከሰቱ አደጋዎች ለህልፈት የሚዳረጉ ሰዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መሆኑን ጠቁሞ፣ በ2014 ተመሳሳይ ወቅት የሞቱት ሰዎች ቁጥር 57 ብቻ እንደነበር አስታውሷል፡፡ በተለይም ከሊቢያ ወደ ጣሊያን የሚዘልቀው የባህር ላይ የጉዞ መስመር እጅግ አስቸጋሪና አደገኛ መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፣ አንድ ጀልባ ከመያዝ አቅሙ በላይ እስከ 600 ስደተኞችን በማሳፈር ረጅሙን የባህር ላይ ጉዞ ለማድረግ እንደሚሞክር ገልጾ፣ በተያዘው የፈረንጆች አመት 2016 ብቻ በአካባቢው 2 ሺህ 119 ሰዎች ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን አስረድቷል፡፡ወደ አውሮፓ የሚደረገው ስደት እየተባባባሰ መምጣቱን የጠቆመው ዘገባው፤ ካለፈው ጥር ወዲህ 204 ሺህ ስደተኞች ሜዲትራኒያን ባህርን አቋርጠው በሰላም ወደ አውሮፓ መግባታቸውን በመግለጽ፣ ባለፈው አመት ተመሳሳይ ጊዜ አውሮፓ የገቡ ስደተኞች ቁጥር 92 ሺህ ብቻ እንደነበር አስታውሷል፡፡

የሪዮ ኦሎምፒክ በዚካ ቫይረስ ሳቢያ መራዘሙን አልተቀበለውም
     የዓለም የጤና ድርጅት የምዕራብ አፍሪካ አገራት ከፍተኛ የጤና ቀውስ ሆኖ የቆየው የኢቦላ ቫይረስ ከፍተኛ ጉዳት ያደረሰባት ጊኒ፣ ከቫይረሱ ነጻ መሆኗን ባለፈው ሰኞ በይፋ ማስታወቁንና በቅርቡ በብራዚል የሚጀመረው የሪዮ ኦሎምፒክ በዚካ ቫይረስ ሳቢያ ለሌላ ጊዜ ይተላለፍ መባሉን እንዳልተቀበለው ተዘገበ፡፡
በጊኒ የኢቦላ ቫይረስን ስርጭት ለመግታትና በቁጥጥር ስር ለማዋል ባለፉት አመታት ሰፊ ርብርብ ሲደረግ መቆየቱን ያስታወሰው የኤቢሲ ኒውስ ዘገባ፤በአገሪቱ ባለፉት 3 ወራት በቫይረሱ ስርጭት ላይ የተቀናጀ ክትትል ሲደረግ እንደቆየና አንድም ሰው በቫይረሱ እንዳልተያዘ መረጋገጡን አስታውቋል፡፡
ይሄም ሆኖ ግን፣ ምንም እንኳን በቫይረሱ የተያዘ አዲስ ታማሚ በአገሪቱ ባይገኝም፣ ቫይረሱ በተለያዩ የሰውነት ክፍሎች ውስጥ በሚገኙ ፈሳሾች ውስጥ ለወራት ተደብቆ የመቆየት ባህሪ ያለው እንደመሆኑ ስርጭቱ ሙሉ ለሙሉ ተገትቷል ማለት እንደማይቻልና ዳግም ሊከሰት እንደሚችል የዓለም የጤና ድርጅት አስጠንቅቋል፡፡
በ2013 በጊኒ የተቀሰቀሰውና ሴራሊዮንና ሊይቤሪያን ወደመሳሰሉ የምዕራብ አፍሪካ አገራት በስፋት የተሰራጨው ኢቦላ ቫይረስ፣ ከ11 ሺህ በላይ ሰዎችን ለህልፈት መዳረጉንም ዘገባው አስታውሷል፡፡
በተያያዘ ዜናም የዓለም የጤና ድርጅት፣ በብራዚል የተቀሰቀሰውና ነፍሰ-ጡሮችን በማጥቃት የተዛባ ጤንነት ያላቸው ህጻናት እንዲወለዱ የሚያደርገው የዚካ ቫይረስ፣ የከፋ የጤና ጉዳት ሊያስከትል ስለሚችል የሪዮ ኦሎምፒክ እንዲሰረዝ ወይም ለሌላ ጊዜ እንዲራዘም ከ150 የተለያዩ የአለማችን አገራት የጤና ኤክስፐርቶች ለተመድ ያቀረቡትን ሀሳብ ውድቅ እንዳደረገው አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
የሪዮን ኦሎምፒክ ለማራዘም የሚያስገድድና የጤና ቀውስ ሊከተል እንደሚችል የሚያሳይ ተጨባጭ ምክንያት የለም፤ ውድድሩን ማራዘምም ሆነ በሌላ አገር እንዲካሄድ ማድረግ፣ ቫይረሱ በአለማቀፍ ደረጃ ያለውን ስርጭት ለመግታት ይህ ነው የሚባል አስተዋጽኦ አያበረክትም ብሏል፤ የዓለም የጤና ድርጅት፡፡

ፕሮጀክቱ የአፍሪካን 40 በመቶ የሃይል ፍላጎት ያሟላል ተብሏል

ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በዓለማችን በትልቅነቱ ቀዳሚውን ስፍራ ይይዛል የተባለውን የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ ግድብ በ14 ቢሊዮን ዶላር ወጪ በጥቂት ወራት ውስጥ መገንባት እንደምትጀምር ተዘገበ፡፡
የአገሪቱ ግዙፍ ፕሮጀክት የመጀመሪያ ክፍል የሆነውና በኮንጎ ወንዝ ላይ የሚገነባው ኢንጋ 3 የተባለው ይህ የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ ግድብ፣ በአምስት አመት ጊዜ ውስጥ ግንባታው ሙሉ ለሙሉ ተጠናቅቆ ሃይል ያመነጫል ተብሎ እንደሚጠበቅ የዘገበው ዘ ጋርዲያን፤4 ሺህ 800 ሜጋ ዋት የማመንጨት አቅም እንዳለውም ጠቁሟል፡፡
ይህ ግዙፍ ግድብ የሚያመነጨው የኤሌክትሪክ ሃይል፣ 20 ትላልቅ የኒውክሌር ሃይል ማመንጫዎች ሊያመነጩት ከሚችሉት ሃይል ጋር የሚመጣጠን ነው መባሉን የጠቀሰው ዘገባው፤የፕሮጀክቱ ቀጣይ አካል የሆነና 40 ሺህ ሜጋ ዋት የማመንጨት አቅም ያለው ሌላ ግድብ በ100 ቢሊየን ዶላር ለመገንባት መታቀዱንም ገልጧል፡፡
የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ ፕሮጀክቱ 40 በመቶ ያህሉን የአፍሪካ የሃይል ፍላጎት ማሟላት ይችላል መባሉን የጠቆመው ዘገባው፤አለማቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾችና የአካባቢ ተቆርቋሪዎች ግን ፕሮጀክቱ በሁለቱም ክፍሎቹ በድምሩ 60 ሺህ ያህል ዜጎችን ያፈናቅላል በሚል እንደተቹት ገልጧል፡፡