Administrator

Administrator

   በቴሌኮም ማስፋፋትና በኔትወርክ ዝርጋታ ስራ የተሰማራው ህዋዌ፤ ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ ለ‹‹መሰረት በጎ አድራጎት›› ድርጅት የትምህርት መሳሪያ ድጋፍ አደረገ፡፡  ድርጅቱ 4500 ደብተሮችን፣ 1500 እርሳሶችን፣ 1500 እስክርቢቶዎችንና ላጲሶችን ለግሷል፡፡ በርክክብ ስነስርዓቱ ላይ ንግግር ያደረጉት የድርጅቱ መስራችና ዳይሬክተር ወ/ሮ መሰረት አዛገ ህዋዌ ስላደረገላቸው ድጋፍ አመስግነው፣ ድጋፉ  ‹‹አንድ እሽግ ለአንድ ልጅ›› በሚል የሚያካሂዱትን የትምህርት ቁሳቁሶች አቅም ለሌላቸው የማከፋፈል ፕሮጄክት፣ በእጅጉ እንደሚያግዛቸው ተናግረዋል፡፡ በዕለቱ ከህዋዌ ያገኙት ድጋፍ በገንዘብ ሲተመን ከ50 ሺህ ብር በላይ እንደሆነ የገለፁት ወ/ሮ መሰረት፤ ድጋፉ ሌሎችም ድርጅቶች ማህበራዊ ሀላፊነታቸውን እንዲወጡ መነቃቃትን ይፈጥራል ብለዋል፡፡
ከድጋፉ ጎን ለጎን መሰረት በጎ አድራጎት ድርጅት የተመሰረተበትን አምስተኛ ዓመት ያከበረ ሲሆን በአምስት አመት ጉዞው ያከናወናቸውን፣ ያሳካቸውንና ያለፋቸውን ፈተናዎች በዘጋቢ ፊልም ለታዳሚዎቹ አቅርቧል፡፡ የህዋዌ ተወካዮችም ድጋፋቸውን እንደሚቀጥሉ በዕለቱ ቃል ገብተዋል፡፡ በመሰረት በጎ አድራጎት ድርጅት ጽ/ቤት በተካሄደው በዚህ ፕሮግራም ላይ ድርጅቱ አምባሳደር አርቲስት ሩታ መንግስተአብና አርቲስት ግሩም ኤርሚያስ እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።

የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር

      የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር ዛይድ ራድ አል ሁሴን በመጪው የአሜሪካ ምርጫ ሪፐብሊካንን በመወከል ለፕሬዚዳንትነት በመወዳደር ላይ የሚገኙት አነጋጋሪው ዕጩ ዶናልድ ትራምፕ አሸንፈው ከተመረጡ አለማችን የከፋ አደጋ ላይ ትወድቃለች ማለታቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
አስፈሪና አሸባሪ አመለካከቶችን የሚያራምዱት ትራምፕ፤ ይህን አቋማቸውን የማይቀይሩና በምርጫው የሚያሸንፉ ከሆነ ለአለማችን ትልቅ ስጋት መሆናቸው አይቀሬ ነው ያሉት ዛይድ፣ በተለይም ትራምፕ ግርፋትን ተግባራዊ ማድረግ አስፈላጊ ነው ማለታቸውንና በተጋላጭ ማህበረሰቦች ላይ ያላቸውን አሉታዊ አመለካከት ክፉኛ ተችተውታል፡፡
በየትኛውም አገር በሚካሄድ ማንኛውም አይነት የፖለቲካ ቅስቀሳ ጣልቃ የመግባት ፍላጎት እንደሌላቸው የገለጹት ዛይድ፣ ግርፋትን በሚያስፋፋና ተጋላጭ ማህበረሰቦችን የሰብአዊ መብቶቻቸው ተጠቃሚ እንዳይሆኑ በሚያደርግ መልኩ የሚቋጭ ምርጫ ሲያጋጥም ግን ዝም ማለት ተገቢ አይደለም ብለዋል፤ባለፈው ረቡዕ ጄኔቫ በሚገኘው የተመድ ዋና ጽ/ቤት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፡፡
ዛይድ በቅርቡ በሄግ ባደረጉት ንግግር ዘረኝነት የተጠናወታቸው አደገኛ ሰው ናቸው ሲሉ የትራምፕንና የሚከተሉትን ፖሊሲ በይፋ ተችተው እንደነበርም ዘገባው አስታውሷል፡፡
በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሩስያ አምባሳደር በበኩላቸው፤ አንድ የተመድ ከፍተኛ የስራ ሃላፊ የውጭ አገራትን መሪዎችና መንግስታትን መተቸት አይጠበቅበትም ሲሉ የኮሚሽነር ዛይድን ንግግር መቃወማቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡

     ባለፈው ሃምሌ ወር ከተቃጣበትና ከከሸፈው የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ጋር በተያያዘ ስፍር ቁጥር የሌላቸው ዜጎቹን ማሰሩን የቀጠለው የቱርክ መንግስት ባለፈው ማክሰኞም ተጨማሪ 125 የፖሊስ መኮንኖችን ማሰሩን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
የፖሊስ መኮንኖቹ እንዲታሰሩ የተወሰነባቸው ባይሎክ የተሰኘውንና በመፈንቅለ መንግስቱ ጠንሳሽ የሆነው ቡድን ደጋፊዎች የሚጠቀሙበትን የአጭር የጽሁፍ መልዕክት ማስተላለፊያ የሞባይል አፕሊኬሽን ሲጠቀሙ ተገኝተዋል በሚል መሆኑን ዘገባው ገልጧል፡፡
የመንግስት ሃይሎች ማክሰኞ ዕለት በመዲናዋ ኢስታንቡል የፖሊስ መኮንኖችንን በቁጥጥር ስር ማዋላቸውን  የጠቆመው ዘገባው፣ ከታሰሩት መካከልም 30 ያህሉ ምክትል የፖሊስ አዛዦች እንደሆኑ ገልጧል፡፡
የአገሪቱን የፍትህ ሚኒስትር ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው ባለፉት ወራት ከከሸፈው መፈንቅለ መንግስት ጋር ንክኪ አላቸው በሚል የተጠረጠሩ 32 ሺህ ያህል የወታደራዊ ሃይል መኮንኖች፣ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት፣ ዳኞች፣ መምህራንና ሌሎች ባለሙያዎች ታስረዋል፡፡

  በህይወት ካሉ የቡድኑ መስራች አባላት አንዱ ነበር

      በህይወት ካሉ ጥቂት የአይሲስ መስራች አባላትና ከፍተኛ አመራሮች አንዱ እንደሆነ የሚነገርለትና የሽብር ቡድኑ የፕሮፓጋንዳ ሃላፊ ሆኖ ሲሰራ የቆየው አቡ ሞሃመድ አል ፉርቃን መሞቱን ቡድኑ በድረ-ገጹ ባወጣው መግለጫ ማረጋገጡን ቢቢሲ ዘግቧል።
የአሜሪካ የመከላከያ ተቋም ፔንታጎን ባለፈው ወር ሶርያ ውስጥ ከምትገኘው ራቃ አቅራቢያ ባደረገው የአየር ጥቃት አቡ ሞሃመድ አል ፉርቃን መግደሉን ቢያስታውቅም፣ አይሲስ ግን ምንም አይነት ምላሽ ሳይሰጥ ቆይቶ በሳምንቱ መጀመሪያ ሞቱን ማረጋገጡን ዘገባው ገልጧል፡፡
ቡድኑ ግለሰቡ መሞቱን እንጂ መቼ፣ የትና እንዴት እንደሞተ ያለው ነገር እንደሌለ የጠቆመው ዘገባው፣ ግለሰቡ የቡድኑን እንቅስቃሴ የተመለከቱ የፕሮፓጋንዳ መረጃዎችን በማዘጋጀትና በማሰራጨት እንዲሁም የቡድኑ ልሳናት የሆኑ ድረ-ገጾችንና መጽሄቶችን በበላይነት በመምራት ይሰራ እንደነበር አስታውሷል፡፡
አቡ ሞሃመድ አል ፉርቃን የአይሲስ የአመራር አካል የሆነው የሹራ ምክር ቤት አባል እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ቡድኑ የግለሰቡን ሞት ያረጋገጠው አንድ የአሜሪካ ተቋም የአይሲስ የፕሮፓጋንዳ ስራ እየተዳከመ መሆኑን በጥናት አረጋግጫለሁ ባለበት ወቅት መሆኑን

 - እየጋየ ያስቸገረውን ይህን ምርቱን በማቆሙ 17 ቢ. ዶላር ያጣል
                       - ደንበኞቹ በአስቸኳይ ስልኩን መጠቀም እንዲያቆሙ አሳስቧል

       በቅርቡ ለገበያ ያቀረበው የጋላክሲ ኖት 7 ምርቱ ባትሪው በቀላሉ የሚግልና እሳት የሚፈጥር ከመሆኑ ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ቀውስ ውስጥ ገብቶ የሰነበተው የደቡብ ኮርያው የቴክኖሎጂ ኩባንያ ሳምሰንግ፣ ችግሩን መፍታት ባለመቻሉ ከአሁን በኋላ ምርቱን ለማቆም መወሰኑን በሳምንቱ መጀመሪያ አስታውቋል፡፡
ኩባንያው በአለም ዙሪያ የሚገኙ ወኪሎቹንና የሞባይል መሸጫ መደብሮችን “ጋላክሲ ኖት 7 መሸጣችሁን አቁሙ፣ እኔም ማምረቴን እስከወዲያኛው አቁሜያለሁ፤ የሸጥኳቸውንም መልሼ እሰበስባለሁ” ሲል መልዕክት ያስተላለፈ ሲሆን፣ ጋላክሲ ኖት 7 ለገዙ ደንበኞቹም እሳት ሊፈጥርና አደጋ ሊያደርስባችሁ ስለሚችል አሁኑኑ መጠቀማችሁን አቁሙ በማለት አስጠንቅቋል፡፡
ባለፈው ወር በምርቱ ላይ የባትሪዎች መቃጠልና መፈንዳት አደጋ መከሰቱን በተመለከተ በርካታ ደንበኞች አቤቱታቸውን ማቅረባቸውን ተከትሎ ኩባንያው በአለም ዙሪያ የሸጣቸውን 2.5 ሚሊዮን የጋላክሲ ኖት 7 ስማርት ፎኖች መልሶ መረከቡን ያስታወሰው ቢቢሲ፤ችግሩን ለመፍታት ያደረገው ጥረት ባለመሳካቱ ምርቱን ማቆሙን ገልጧል፡፡ ጋላክሲ ኖት 7 የገዙ ደምበኞች የከፈሉት ገንዘብ እንደሚመለስላቸው አልያም በምትኩ ሌላ የፈለጉት የጋላክሲ ስማርት ፎን ሊቀየርላቸው እንደሚችል ኩባንያው ማስታወቁን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ሳምሰንግ ጋላክሲ ኖት 7 ማምረት ማቆሙን በይፋ ማስታወቁን ተከትሎ የኩባንያው የአክስዮን ድርሻ 8 በመቶ ቅናሽ ማሳየቱንና በዚህም 20 ቢሊዮን ዶላር ማጣቱ የተነገረ ሲሆን፣ ኩባንያው በጋላክሲ ኖት 7 ቀውስ 17 ቢሊዮን ዶላር ያህል ገቢ ሊያጣ ይችላል መባሉንም አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡ ኩባንያው በአመቱ አራተኛ ሩብ አመት 500 ቢሊዮን ዶላር ትርፍ አገኛለሁ ብሎ አቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ ትርፉ በ85 በመቶ ሊቀንስ እንደሚችልና በመጪው 2017 ከሞባይል ገበያ አገኘዋለሁ ብሎ ያቀደው ትርፍም በ22 በመቶ ሊቀንስ እንደሚችል ባለሙያዎች ትንበያቸውን ሰጥተዋል፡፡
በጋላክሲ ኖት 7 ስማርት ፎኖች ላይ የታየው ችግር ኩባንያው በአለማቀፉ የስማርት ፎን ገበያ ያለውን ተቀባይነት ክፉኛ እንደሚጎዳውና የደንበኞቹን አመኔታ እንደሚያሳጣው የዘርፉ ተንታኞች መናገራቸውን የጠቆመው ቢቢሲ፣ የደቡብ ኮርያው የፋይናንስ ሚኒስትርም ኩባንያው ምርቱን ማቆሙ በወጪ ንግዱ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ እንደሚፈጥር መናገራቸውን አስታውቋል፡፡ የአለማችንን የስማርት ፎን ገበያ 98.7 በመቶ ድርሻ የያዙት ሳምሰንግ እና አፕል ኩባንያዎች እንደሆኑ የዘገበው ዘ ስትሪት ድረገጽ በበኩሉ፣ የሳምሰንግ ወቅታዊ ቀውስ ለተፎካካሪው አፕል መልካም ዕድል እንደሚሆን መነገሩን ጠቁሟል፡፡

የኢስቶኒያ መንግስት ላቋቋመው ግዙፍ የሃይል ማመንጫ ተቋም በግብዓትነት የሚውል ቆሻሻ እጥረት በማጋጠሙ ከውጭ አገራት ከፍተኛ መጠን ያለው ቆሻሻ እየገዛ እንደሚገኝ ቢቢሲ ዘገበ፡፡
አገሪቱ ከቆሻሻ ሃይል ለሚያመነጨውና ኢሩ በተባለው አካባቢ ለሚገኘው ተቋም በቂ የሆነ ቆሻሻ በአገር ውስጥ ማግኘት ስላልቻለች፣ ከተለያዩ አገራት ቆሻሻ ለመግዛት መገደዷን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፈው አመት ብቻ 56 ሺህ ቶን ቆሻሻ ከውጭ አገራት ገዝታ እንዳስገባች ገልጧል፡፡
የሃይል ማመንጫው ባለፈው አመት ብቻ 245 ሺህ ቶን ቆሻሻ በጥሬ እቃነት መጠቀሙንና በአገር ውስጥ በቂ ቆሻሻ ባለመገኘቱ ሳቢያ ስራ ሊያቆም የሚችልበት ደረጃ ላይ በመድረሱ የአገሪቱ መንግስት ቆሻሻን ከውጭ አገራት በመግዛት ስራውን ለማስቀጠል መወሰኑንም ዘገባው አስታውሷል፡፡
ለኢስቶኒያ መንግስት ቆሻሻ በመሸጥ ላይ ከሚገኙ አገራት መካከል ፊንላንድና አየርላንድ ይገኙበታል ያለው ዘገባው፣ ቆሻሻን ከውጭ አገራት ገዝቶ በማስገባት ሃይል የማመንጨት ኢንቨስትመንቱ አዋጪ እንደሆነ አንድ የአገሪቱ ባለስልጣን መናገራቸውንም አክሎ አስታውቋል፡፡

1 ቢሊዮን ዶላር ያህል ይፈጃል ተብሏል

    የአለማችን ረጅሙ ሰማይ ጠቀስ ህንጻ የሆነው ቡርጂ ከሊፋ መገኛ የሆነቺው ዱባይ በእርዝማኔው አቻ የማይገኝለት ይሆናል የተባለውን ማማ መገንባት መጀመሯን በሳምንቱ መጀመሪያ አስታውቃለች፡፡
ኢማር ፕሮፐርቲስና ዱባይ ሆልዲንግ የተባሉት ሁለት ኩባንያዎች በጋራ የሚያሰሩት አዲሱ ማማ ግንባታው በአራት አመታት ጊዜ ውስጥ እንደሚጠናቀቅ የዘገበው ሮይተርስ፣ማማው ምን ያህል እንደሚረዝም ግልጽ መረጃ አለመውጣቱን ገልጧል፡፡
ይሄም ሆኖ ግን ግንባታው የተጀመረው ማማ፣ 829.8 ሜትር ከሚረዝመው የአለማችን ቁጥር አንድ ሰማይ ጠቀስ ህንጻ ቡርጂ ከሊፋ የሚበልጥ እርዝማኔ እንደሚኖረው መረጃዎች መውጣታቸው እየተነገረ ሲሆን፣ ኢማር ፕሮፐርቲስ ባለፈው ሚያዝያ ወር ላይ በሰጠው መግለጫ ለማማው ግንባታ 1 ቢሊዮን ዶላር ያህል ወጪ እንደሚደረግ ማስታወቁን ሲቢቢ የዜና ወኪል አስታውሷል፡፡
ማማውን ዲዛይን ያደረገው ስፔናዊው አርክቴክት ሳንቲያጎ ካላትራቫ ቫልስ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ የከተማዋን ሙሉ ገጽታ ማሳየት የሚችል መሆኑንም አስታውቋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በአለማችን ረጅሙን ማማ ሆኖ የተመዘገበው በቶክዮ የሚገኘው ስካይ ትሪ የተባለው ማማ ሲሆን፣ 634 ሜትር ቁመት እንዳለው ዘገባው ገልጧል፡፡

 ሁዋዌ ስመጥር የስዊዝ ዲዛይን ስሪትና የስማርት ቴክኖሎጂን በማጣመር የተፈበረከ፣ የላቀ የስክሪን ጥራት ያለው ዘመናዊ የእጅ ሰዓት ለገበያ አቀረበ፡፡
ዓይንን በሚስብ ገፅታ በዘርፉ አንጋፋ በሆኑ ባለሙያዎች በጥንቃቄ የተፈበረከው ሁዋዌ የእጅ ሰዓት፤ በአዳዲስ የሰዓት ቴክኖሎጂዎችና ከፍተኛ አቅም ባላቸው ጥሬ ዕቃዎች ተሰርቶ ለገበያ የቀረበ ሲሆን የነባሩን የእጅ ሰዓት አሰራር በአዲስ ቴክኖሎጂ በማራቀቅ ዘመኑን የሚወክል ምርት ነው ተብሏል፡፡
የሁዋዌ አዲሱ የእጅ ሰዓት የዕለት እንቅስቃሴዎን ማገዝ በሚችሉ ቴክኖሎጂዎች የተሞላ ሲሆን ተጠቃሚዎች እጅ ላይ በማሰር በማንኛውም እንቅስቃሴ ወቅት ሊጠቀሙበት የሚችሉት ነው፡፡ በተገጠመለት እንቅስቃሴን የሚለይ ቴክኖሎጂ አማካኝነት ተጠቃሚዎች በሚራመዱበት፣ በሚሮጡበት አልያም ተራራ በሚወጡበት ጊዜ የሰውነት እንቅስቃሴ መለየት እንደሚያስችልም ተነግሯል፡፡
ሁዋዌ የእጅ ሰዓት የአንድሮይድ ቴክኖሎጂን የሚጠቀም ሲሆን ተጠቃሚዎች የሚሹትን ወቅታዊ መረጃዎች የሚያገኙበት እንደሆነ ታውቋል፡፡ የእጅ ሰዓቱ ሙዚቃ፣ አፕሊኬሽኖችንና ጎግልን ጭምር መጠቀም የሚያስችል ቴክኖሎጂ አለው ተብሏል፡፡

ሽልማቱን ያሸነፈ የመጀመሪያው የዘፈን ግጥም ደራሲ ነው

የ75 ዓመቱ የሮክ ሙዚቃ አቀንቃኝ አሜሪካዊው ቦብ ዳይላን በዘፈን ግጥሞች ደራሲነቱ የ2016 የሥነ ፅሁፍ የኖቤል ሽልማት አሸናፊ ሆነ፡፡ “በታላቁ የአሜሪካውያን የዘፈን ባህል ውስጥ አዲስ ቅኔያዊ አገላለፅ በመፍጠሩ ነው” ለሽልማቱ የበቃው ተብሏል።
እ.ኤ.አ በ1993 ዓ.ም የረዥም ልብ ወለድ ደራሲው ቶኒ ሞሪሰን የሥነ ፅሁፍ የኖቤል ሽልማት ከወሰደ በኋላ ይሄን ሽልማት ያሸነፈ የመጀመሪያው አሜሪካዊ ሆኗል፤ ቦብ ዳይላን፡፡ ይሄን እጅግ የተከበረ ሽልማት ያሸነፈ የመጀመሪያው የዘፈን ግጥም ደራሲም ነው ተብሏል፡፡
ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ሽልማቱን በተመለከተ በሰጡት አስተያየት፤ “በጣም ይገባዋል›› ብለዋል። “ከምወዳቸው ገጣሚያን አንዱ የሆንከው ገጣሚ፣ እንኳን ደስ ያለህ” ሲሉ በትዊተራቸው ላይ አስፍረዋል - ኦባማ፡፡ የስዊዲሽ አካዳሚ ዋና ፀሐፊ ሳራ ዳኒዩስ፤ ቦብ ዳይላን ለሽልማቱ የተመረጠው “በእንግሊዝኛ ተናጋሪው ማህበረሰብ ዘንድ ታላቅ ገጣሚ ስለነበር ነው” ብለዋል፡፡
“ለ54 ዓመት ያህል በሙያው ውስጥ ራሱን ሲፈጥር ኖሯል፤ ያለማቋረጥ አዲስ ማንነት በመፍጠር” ሲሉ ሳራ ዳኒዩስ፤ ለሪፖርተሮች ተናግረዋል፡፡

“የስልጣን ፍላጎት የሌለው አካል መቋቋም አለበት”
አቶ ወንድወሰን ተሾመ (የኢዴፓ አመራር)
የነዚህ ቀውሶች መነሻ ምክንያቶች በርካታ ናቸው፡፡ ወደ መፍትሄው ለመሄድ ከተፈለገ ግን የፖለቲካ ስልጣን ፍላጎት የሌለው አካል መቋቋም አለበት፡፡ ውይይቶች በስፋት ከተደረጉ ብዙ ችግሮች ሊፈቱ ይችላሉ፡፡ መንግስት አሁን ባለው ሁኔታ በመደበኛ ተግባሩ ላይ ቀጥሎ ሂደቱ መካሄድ አለበት እንጂ የሽግግር መንግስት ምናምን የሚለው የማያስኬድ ነው፡፡ ለስልጣን ፍላጎት የሌለው ገለልተኛ አካል ተቋቁሞ፣ ብሄራዊ እርቅ ላይ ጠንከር ተብሎ መሰራት አለበት፡፡ “መንግስት የመፍትሄው አካል መሆን የለበትም፣ የሽግግር መንግስት ይቋቋም” በሚለው ሃሳብ አልስማማም፡፡ የሽግግር መንግስት ይቋቋም ቢባል ማን ነው የሚያቋቁመው? ስለዚህ አንድ ነፃ አካል የግዴታ መቋቋምና ሃሳቦች የሚንሸራሸሩበትን እድል መክፈት ያሻል እንጂ ይህ ስርአት እንደወደቀ አድርጎ የሽግግር መንግስት መቋቋም አለበት የሚለው እኔ ብዙም አይታየኝም፡፡

===========================

“ተቃውሞ የሚገታው ጥያቄዎችን በመመለስ ነው”

በላይ ማናዬ (ጋዜጠኛና ጦማሪ)
በኔ ግምት የተቃውሞዎቹ መነሻ የመብት ጥያቄዎች ናቸው፡፡ ህዝቡ የመብት ጥያቄ ማንሳቱ ደግሞ የተነፈጉ መብቶች መኖራቸውን ነው የሚያመለክተው፡፡ ጥያቄዎቹ በሰላማዊ መንገድ ነበር የተጀመሩት፡፡ መንግስትም ህገ መንግስታዊ ናቸው ብሎ ያመነበት ሁኔታ ነበር፡፡ በተለይ የማስተር ፕላኑን ጉዳይ በተመለከተ በአግባቡ እያወያዩ ለህዝቡ ምላሽ በመስጠት ረገድ የታየው ዳተኝነት የችግሩ መነሻ እንደነበር መንግስት ራሱ ሲገልፅ ነበር፡፡ ስለዚህ በኔ እምነት የእነዚህ ሁሉ ተቃውሞዎች መነሻ ህዝቡ የተነጠቀው መብት መኖሩ ይመስለኛል።
መንግስት ለነዚህ ተቃውሞዎች ምላሽ የሰጠበት መንገድ አጥጋቢ ነው ብዬ አላስብም፡፡ በተለይ በሰለጠነ መንገድ ይበልጥ ውይይቶችን እየፈቀደ፣ የህዝብን ጥያቄ ለመመለስ ያደረገው ጥረት ዝቅተኛ ነው፡፡ ለዚያም ነው ተቃውሞዎቹ እየበረቱ የሄዱት። የህዝቡ ተቃውሞ አሁን በያዘው ቅርፅና መልክ ወደተለያዩ ቦታዎች ሳይዳረስና ሳይስፋፋ፣ከህዝቡ ጋር በሰፊው ተነጋግሮ መፍትሄ ለመስጠት ይቻል ነበር ብዬ አምናለሁ፡፡ በእርግጥ የተቃውሞ ድምፆች በፓርላማው ሊኖር ይገባ ነበር፡፡ የህዝብ መተንፈሻ መኖር ነበረበት፡፡  ይህ በሌለበት ሁኔታ የታመቀ ነገር ይኖራል፡፡ የታመቀ ነገር ደግሞ ይፈነዳል፡፡ አሁን እያየን ያለነው እንዲህ ያለውን ነገር ነው፡፡
የዘገዩ ነገሮች እንዳሉ ባምንም አሁንም ቢሆን በትልቁ መፍትሄውን ማሰብ እንችላለን፡፡ ሁሉን አቀፍ ለውጥ የሚያመጣ መድረክ አዘጋጅቶ በውይይት መቀራረብ ያሻል፡፡
መንግስት ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ተነጋግሮ መፍትሄ ሊያበጅ ይችላል። የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ረጅም ጊዜን ይወስዳል። በነዚህ ጊዜያት መንግስት የበለጠ ከህዝቡ ጋር መወያየትና ህዝቡን አዳምጦ ተገቢ ምላሾችን ሊሰጥ ይገባል፡፡ የተቃውሞዎቹ መግቻ ነው ብዬ የማምነው፣ከስር ከስር ጥያቄዎችን እየመለሱ መሄድ ነው፡፡  

============================

“የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁም ወደ መፍትሄው የሚወስደን መሆን አለበት”
ጁሃድ ሳዲቅ  (የጋዜጣ አምደኛ)

በእኔ እይታ አሁን ያለው ተቃውሞ ዋናው መንስኤ የዲሞክራሲ እጦት ነው፡፡ የመናገር፣ ሃሳብን የመግለፅ የመሳሰሉት መብቶች በሚገባ  በተግባር ላይ አልዋሉም፡፡ የፕሬስ ነፃነቱም በሚገባ አልተተገበረም። ዲሞክራሲ ሳይኖር ደግሞ ሰላምና መረጋጋት ሊኖር አይችልም፡፡ የሁሉም ነገር ዋና ማዕከል ዲሞክራሲ ነው፡፡ መንግስት ዲሞክራሲን ረስቶታል ማለት እንችላለን፡፡ ሁልጊዜ ስለ ልማት ብቻ ነው የሚነሳው፡፡ እርግጥ ልማትን ሁሉም ይደግፈዋል፤ ለሀገራችን እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ ትልቁ ክፍተት ዲሞክራሲን ከልማት ጋር በሚገባ ማያያዝ አለመቻሉ ነው፡፡ መንግስት ለዚህ ቶሎ መፍትሄ መስጠት አለበት፡፡ ሌላው የፕሬስ ነፃነትን የተመለከተ ነው፡፡ በቅርቡ ሶሻል ሚዲያውን ዘግቷል። ያሉት ፕሬሶች መንግስት የሚገልፀውን ብቻ ዋቢ አድርገው የሚጠቀሙ ናቸው፤ ራሳቸው አጀንዳ ቀርፀው አይሰሩም። ህብረተሰቡ ከነሱ ያጣውን ለማግኘት ወደ ማህበራዊ ሚዲያው አዘንብሏል፡፡ የትኛውም ሰው ሃሳቡን የሚገልጽበት ነፃ መድረክ ሆኗል፡፡ ውጭ ሀገር ሆነው የሚፅፉ ሰዎች አሉ፡፡ ሰው የነሱን ሀሳብ ይከተላል፡፡ ለዚህ መፍትሄው መንግስት ፕሬሱን በሰፊው መክፈት ነው፡፡
በሌላ በኩል የምርጫ ስርአት መስተካከል አለበት። ተቃዋሚዎች የህዝብ ወኪልና ጆሮ እንደመሆናቸው ህዝባቸውን የሚወክሉበት በቂ ቦታ ማግኘት አለባቸው፡፡ አለበለዚያ የወሰዱት የህጋዊነት ፍቃድ የግድግዳ ላይ ጌጥ ይሆናል ማለት ነው፡፡ አሁንም መንግስት ወደ ድርድርና ንግግር መምጣት አለበት፡፡ ለተቃዋሚ ፖለቲከኞች ሰፊ መድረክ መስጠት አለበት፡፡ ለሀገር ውስጥ ተቃዋሚ ቦታ የማይሰጥ ከሆነ፣ ማህበረሰቡ ውጭ ወዳለው ተቃዋሚ ያዘነብላል፡፡ ውጭ ሀገር ያለው የፖለቲካ ቡድን ሀገር ውስጥ ካለው ጋር ብዙ ግጭቶች አሉበት፡፡ ህዝቡ ግን አማራጭ ሲያጣ ወደነሱ ይሄዳል፡፡ ስለዚህ ተቃዋሚዎችን በሚገባ አቅርቦ መወያያት አለበት፡፡
ሌላው ተቃውሞዎቹ በሙሉ የመንግስት የመልካም አስተዳደር ችግሮች ነፀብራቅ ናቸው። ከሙስሊሙ ማህበረሰብ ጥያቄ ጀምሮ እስካሁን ያለውን ችግር በጠረጴዛ ዙሪያ መፍታት እየተቻለ ወደ ሌላ አቅጣጫ ነው የተመሩት፡፡ የመንግስት ኮሚኒኬሽን ሃላፊዎችም እርስ በእርሱ የተምታታ መረጃ ነበር ለህዝቡ ሲያስተላልፉ የነበሩት። በኦሮሚያ ኦፌኮ በተደጋጋሚ ማስተር ፕላኑን በተመለከተ እንወያይ የሚል ጥሪ አድርጓል፤መንግስት ግን ምላሽ ሳይሰጥ ቆይቶ በመጨረሻ ነው ማስተር ፕላኑን ሰርዣለሁ ያለው። ይሄን ካለ በኋላ ደግሞ በወቅቱ ከዚሁ ጉዳይ ጋር በተያያዘ የታሰሩት መፈታት ነበረባቸው። እነዚህ ሰዎች ማስተር ፕላኑን ነበር የተቃወሙት፤ ስለዚህ ሊፈቱ ይገባ ነበር፡፡ ለሟች ቤተሰቦችና ንብረት ለወደመባቸው ካሳ መክፈል ነበረበት፡፡ መንግስት ይቅርታ የጠየቀባቸውን ነገሮች በሚገባ ማስተካከል ሲገባው ዳተኝነት አሳይቷል፡፡  
አሁንም ከዚህ በኋላ ገዥውም ተቃዋሚውም ግልፅ ፖለቲካን ያራምዱ፡፡ የህብረተሰቡን ችግር ይስሙ፣ ይረዱ፡፡ እንደ አለመታደል ሆኖ አገራችን ሙሉ ሰላም ያገኘችበት የታሪክ አጋጣሚ የለም፤ ይሄ ያሳዝናል። ባለንበት ዘመን ይሄ መለወጥ አለበት፡፡ በውይይትና በምክክር ችግሮችን የመፍታት ባህል መዳበር አለበት። ሰው በመረጃ መበልፀግ አለበት። የተበላሸው የሚዲያ ምህዳር መስተካከል አለበት። መንግስት ችግሩን ብቻውን ለመፍታት መታገል የለበትም፡፡
ሁሉም የመፍትሄ አካል መሆን አለበት። ህዝቡ ስለሃገሩ ሁኔታ የማወቅ፣የመቆርቆር መብቱ ሊከበርለት ይገባል፡፡
ተቃዋሚዎች ወደ ፓርላማ የሚገቡበት ሁኔታ መኖር አለበት፡፡ መንግስት፤ ህዝብ ዝም ቢልም እየታዘበው መሆኑን ማወቅ አለበት፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁም በሚገባ ወደ መፍትሄው የሚወስደን መሆን አለበት እንጂ ይበልጥ የሚያፍን መሆን የለበትም፡፡