Administrator

Administrator

Saturday, 14 April 2018 14:47

ጲላጦስ

  (የፍርደ ገምድሎች እንጦሮጦስ!)
        ይህን ሰው ስለ ምን ትከሱታላችሁ? አላቸው። (ዮሐ. 18፡29)
        በዚህ ሰው አንድ በደል ስንኳ አላገኘሁበትም አለ። (ሉቃስ 23፡4)

    (ካለፈው የቀጠለ)
3 - ዥዋዥዌ
በእርግጥም ጲላጦስ አለቅጥ እንዲንገጫገጭ ሆኖ ነበር...
  . . . አስቀድሞ ፤ (ዮሐ. 18፡31-32) . . . እናንተ ወስዳችሁ እንደ ሕጋችሁ ፍረዱበት አላቸው። አይሁድም ለእኛስ ማንንም ልንገድል አልተፈቀደልንም አሉት፤ ኢየሱስ በምን ዓይነት ሞት ሊሞት እንዳለው ሲያመለክት የተናገረው ቃል ይፈጸም ዘንድ ነው። (ወንጀለኞችን በስቅላት ቅጣት መግደል ሮማዊያኑ ወደ ቅድስቲቱ ምድር ያመጡት አዲስ ባህል በመሆኑ፤ የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር - የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ገጽ 82 - ስቅለት - ነገር ግን እስራኤላውያን ሰውን በስቅላት አይገድሉም ነበር፤ ዘዳ 21፡21-23/ኢያሱ 10፡26)
በኋላም፤ ጲላጦስ ‹‹የአይሁድን ንጉሥ ልፈታላችሁ ትወዳላችሁን?›› ብሎ አማራጭ ሲያቀርብም፤ እግረ መንገድ አሁንም ከኢየሱስ ያጣውን ምላሽ ለማሟላትና ያንኑ ሮማዊያኑን የሚያባትታቸውን የንጉሥነቱን ጉዳይ ከሕዝቡም እያውጣጣ (investigate እያደረገ) ነበር፡፡ በተለይም በዮሐንስ ወንጌል እንደምናነበው፤ ጲላጦስ የኢየሱስን ፖለቲካዊ ‹አዝማሚያ› ለማወቅ አስልቶ ነበር ይላሉ፤ የታሪክ ተመራማሪያኑ፡፡ Pilate carefully questioned the prisoner about His political roll.
እውነትም ከዚያ ሁሉ ጥያቄና መልስ በኋላ አሁንም ለኢየሱስ ያንኑ ጥያቄ ደግሞ ያቀርብለታል . . .
ጲላጦስም፡- እንግዲያ ንጉሥ ነህን? አለው። ኢየሱስም መልሶ፦ እኔ ንጉሥ እንደ ሆንሁ አንተ ትላለህ። እኔ  ስለ እውነት ልመሰክር ስለዚህ ተወልጃለሁ ስለዚህም ወደ ዓለም መጥቻለሁ፤ ከእውነት የሆነ ሁሉ ድምፄን ይሰማል አለው። ጲላጦስ፡- እውነት ምንድር ነው? አለው። (ምናልባት የጲላጦስ እውነት ንጉሡን ከማገልገል ያለፈ ስላልነበረ ይሆንን?) ይህንም ብሎ ዳግመኛ ወደ አይሁድ ወጥቶ እኔስ አንዲት በደል ስንኳ አላገኘሁበትም። ነገር ግን በፋሲካ አንድ ልፈታላችሁ ልማድ አላችሁ፤ እንግዲህ የአይሁድን ንጉሥ ልፈታላችሁ ትወዳላችሁን? አላቸው። ሁሉም ደግመው በርባንን እንጂ ይህን አይደለም እያሉ ጮኹ። በርባን ግን ወንበዴ ነበረ። (ዮሐ. 18፡37-40) እርሱም በፍርድ ወንበር ተቀምጦ ሳለ፣ ሚስቱ ስለ እርሱ ዛሬ በሕልም እጅግ መከራ ተቀብያለሁና በዚያ ጻድቅ ሰው ምንም አታድርግ ብላ ላከችበት። (ማቴ.27፡13-19) (ጲላጦስ ግን የሚስቱን ምክር አልሰማም፡፡ ሆኖም ግን አሁንም በኢየሱስ ላይ ለመፍረድ ዝግጁ አይደለምና ደግሞ ይጠይቃል) በርባንን ወይስ ክርስቶስ የተባለውን ኢየሱስን ማንኛውን ልፈታላችሁ ትወዳላችሁ? አላቸው፤ በቅንዓት አሳልፈው እንደ ሰጡት ያውቅ ነበርና። (ግን ይህን ራሱ የሚያውቀውንም ውስጡን አልሰማም)... በዚህ ሰው አንድ በደል ስንኳ አላገኘሁበትም አለ። (ሉቃስ 23፡4) ገዢውም፤ ምን ነው? ያደረገው ክፋት ምንድር ነው? አለ (ማቴ. 27፡23)
(እስከ መጨረሻው ቅጽበት ኢየሱስን ሊፈታው መፈለጉን እናስተውላለን፤ግና እርሱ ራሱ የወደደውንም አላደረገም፡፡ ወደ መጨረሻም ከከሳሾቹ ድምጽ ውስጥ ያስተጋባው አንዳች አስገምጋሚ ምላሽ ሳያናውጠው አልቀረም፡፡)
...ራሱን የእግዚአብሔር ልጅ አድርጎአልና አሉት። ስለዚህ ጲላጦስ ይህን ነገር በሰማ ጊዜ እጅግ ፈራ፤ ተመልሶም ወደ ገዢው ግቢ ገባና ኢየሱስን አንተ ከወዴት ነህ? አለው። ኢየሱስ ግን አንድ እንኳ አልመለሰለትም። ስለዚህ ጲላጦስ አትነግረኝምን? ልሰቅልህ ሥልጣን እንዳለኝ ወይም ልፈታህ ሥልጣን እንዳለኝ አታውቅምን ? አለው። ኢየሱስም መልሶ፦ ከላይ ካልተሰጠህ በቀር በእኔ ላይ ምንም ሥልጣን ባልነበረህም፤ ስለዚህ ለአንተ አሳልፎ የሰጠኝ ኃጢአቱ የባሰ ነው አለው። ከዚህ በኋላ ጲላጦስ ሊፈታው ፈለገ፤ ነገር ግን  . . . (ዮሐ. 19፡7-12)
(ፍፁም ባልጠበቀው መንገድ በስጋት የሚንጥና የሞት ፍርድ ውሳኔውን ከማሳለፍ ወዴትም ውልፍት ማለት የማያስችለው ወጥመድ ፊቱ ተደቀነበት! . . .)
...ይህንስ ብትፈታው የቄሣር ወዳጅ አይደለህም፤ ራሱን ንጉሥ የሚያደርግ ሁሉ የቄሣር ተቃዋሚ ነው እያሉ ጮኹ።
በርግጥም ያኔ፤ ጲላጦስ ክፉኛ ክው ያለ እናም በቃ በእጅጉ የተንገጫገጨ አሳዛኝ ሰው የሆነ ይመስላል፡፡ በደካማ ጎኑ ነበር የመጡበት፡፡ አዎን! ማንም ቢሆን በዚህ መሰል ሁኔታ ውስጥ ራሱን ቢያገኘው፤በዚያች ወሳኝ ፍትሀዊ የፍርድ ውሳኔ የማሳለፊያ ቁርጥ ጊዜ ላይ በፍርድ ወንበሩ ቢቀመጥ ላፍታም ቢሆን  ይዋልላል፡፡ ግን ደግሞ ሁለት አማራጭ ይኖረዋል፤ ወይ ከአለት የጸና የልዕለ ሰብዕና ካባ የሚያጎናጽፈውን እውነት ጠብቆ ለእውነቱና ለራሱ ህሊና ታማኝ መሆን ይችላል ወይም ደግሞ ህሊናውን እየቧጠጠ ለሚያደማ ሀሰት ተገዝቶ፣ የአዕምሮ እረፍቱን አሟጥጦ ደፍቶ፣ ሰላምና ክብሩን አጥቶ፣ እስከ ዘላለሙ ንፁህ ሰብእናውን አጉድፎ ከራሱ ከማንነቱና ከመላው ሕዋ ጋርም ተቆራርጦ ያርፈዋል። ውሳኔው ቀላል አይደለም፡፡ እናስ እሺ ጲላጦስ ምን ሊል ይችላል... ‹‹አሁን ባይኔ መጣሽ!››  እንዴ! ለምን ምንም ነገር ጥንቅር ብሎ አይቀርም፤የንጉሡን ወዳጅነት አጥቶ ከመኖር፡፡ ህእ!›› (‹‹የምኖረው ለማን ሆነና!›› አይነት፡፡)
...በዚህ አተያይ/ መላምት ዙሪያ ያጠነጠኑት የታሪክ ተመራማሪዎቹም ይህን አሻሚ የኢየሱስ ከሳሾች አቀራረብ፤ የጲላጦስን የዳኝነት አቋም እሁለት ቦታ የከፈለ (explicit threat against Pilate) ፈተና ነበር ይሉታል ፡፡
ጲላጦስ፤ በኢየሱስ ላይ ባሳለፈው ፍርዱም ለንጉሡ ስሞታ ቀርቦበት እንደለመደው ከምርመራ ጥያቄ ቢያመልጥም፤ በኋለኞቹ ተደጋጋሚ ስህተቶቹ ምክንያት ግን ወደ ሮማ መጠራቱ አልቀረለትም፡፡
4 - የፍርድ ጥፍር
‹‹ህማማት ነውና የይሁዳን ታሪክ ልንገርህ...›› ይለናል፤ የኔታ ስብሀት ለአብ ገብረ እግዚአብሔር በ567 ድርሰቱ ውስጥ አምስት ልጆቹንና ስድስተኛ ሚስቱን በረሀብ ሞት ተነጥቆ፣ 7ኛ አንድ እሱ ብቻውን ቀርቶ እብደት ባናወዘውና ታማኙን የእርሻ በሬውን አርዶ በመብላቱ ራሱን በአስቆሮቱ ይሁዳ በመሰለው ገጸ ባሕርይው አንደበት፡፡... ‹‹ ይሁዳ ከዳተኛ ነው ይላሉ፣ የኔን ታሪክ ያልሰሙ፡፡ ይሁዳ እንኳ ተጸጸተ፤ ተሰቀለ፤ ራሱን ገደለ፤ እኔ ግን! እኔ ግን! ወይኔ! ወይኔ! ወይኔ!
ይህ ድምጽ በሀገረ ገዢው፣ በተንገጫገጨው ዳኛ ልቦናም ውስጥ ያለማቋረጥ መጎሰሙ አይጠረጠርም፡፡
ጲላጦስ፤ ከቄሣሩ ጋር ሲገናኝ የቀረቡበትን ስሞታዎች ሁሉ በወዳጅነት መንፈስ ሊያስተባብል ይቻለዋልና እምብዛም አያሳስበውም፤ ምናልባትም በታማኝነትና ፍጹም ታዛዥነት ለአስር ዓመታት በጽናት ላበረከተው አገልግሎቱ ከንጉሡ ዘንድ ውዳሴና ሹመትም ሳይጠብቅ አይቀርም፡፡ አሳዛኙ ነገር ግን ጲላጦስ ሀገሩ ሲደርስ፤ እንዲያ አቅሉን እስኪስት ጠብ እርግፍ ያለለት ጌታው ጢባርዮስ ቄሣር ሞቶ ነበር። ይህም ብቻ አይደል፤ ጲላጦስ ገፍቶት/ ሰቅሎት የመጣው ክርስትናም ትንሣኤ አድርጎ በራሱም ምድር ዙሪያ ቀድሞት መድረሱንና ዘሩ ማጎንቆል መጀመሩን በገነገነ ጊዜ፤ (በጲላጦስ ፊት የካዳችሁትን ብላቴናውን ኢየሱስን አከበረው። ሐዋ.3፡13) በምርመራው ፍጻሜ በVienna-on-Rhone  በግዞት ሳለ ፤ ሁለመናውን እንደ ረመጥ እየፈጀ እሚያብከነክነው በኢየሱስ ላይ ያሳለፈው ፍርድ ሌት ተቀን እረፍት ስለነሳው፤  ጲላጦስም የከሀዲውን የይሁዳን ጽዋ ጨለጣት፡፡ ... ኢየሱስን አሳልፎ የሰጠው ይሁዳ እንደ ተፈረደበት አይቶ ተጸጸተ፥...ብሩንም በቤተ መቅደስ ጥሎ ሄደና ታንቆ ሞተ። (ማቴ. 27:3/5) ጲላጦስም እንዲሁ ‹‹የቤተ መንግሥት ክብሩን ጥሎ›› ራሱን ገደለ፡፡
ከቶ አይቀርም ሞቱ
ምንም ቢታክቱ
ምን ቢሰነብቱ፡፡
 (የሕዝብ ግጥም - በገና፡፡)
5 - ባርነት ወ ነጻነት
‹‹ሰማይና ምድር ያልፋሉ ቃሌ ግን አያልፍም።›› እንዲል መጽሐፍ፤ አልፋና ኦሜጋ ኗሪው ህያው ቃል፣ ስለ ፍጥረት ባርነት እና ስለ እግዚአብሔር ነጻነት፣ ክብር፣ተስፋ፣ ምህረት፣ ሕግ እና ፍርድ ...ያበረከተልንን የሕይወት ስንቅ አስታውሰን እናሳርግ ...ሰዎች ነንና ከኃጢዐት ፈተና ባናመልጥም፣ እንደ ስራችን ሳይሆን እንደ ፀጋና ቸርነቱ ማስተዋሉን ቢያድለን እንማርበት ዘንድ፤ ከልብ እውነቱ የተፋታ፣ ለሌሎች በባርነት ተኮድኩዶ፣ ላላመነበት እውነት አጎብድዶ ራሱን የካደ ሰው ያመሻሽ እድሜ ዘመን እርቃኑን ሲቀር ምን እንደሚመስል የምስኪኑ ፈራጅ አሳዛኝ ገድል ጥሩ ማሳያ ነውና ከጲላጦስ ከንቱ ፀፀት ያትርፈን፡፡ ሁሉ ከንቱ ከንቱ፡፡ እነሆ . . . (ሮሜ  8:20-21) ፍጥረት ለከንቱነት ተገዝቶአልና፥ በተስፋ ስላስገዛው ነው እንጂ በፈቃዱ አይደለም፤ ተስፋውም ፍጥረት ራሱ ደግሞ ከጥፋት ባርነት ነጻነት ወጥቶ ለእግዚአብሔር ልጆች ወደሚሆን ክብር ነጻነት እንዲደርስ ነው። (ገላትያ 5፡1) በነጻነት ልንኖር ክርስቶስ ነጻነት አወጣን፤ እንግዲህ ጸንታችሁ ቁሙ እንደ ገናም በባርነት ቀንበር አትያዙ። (የያዕቆብ መልእክት 2፡12-13) በነጻነት ሕግ ፍርድን ይቀበሉ ዘንድ እንዳላቸው ሰዎች እንዲህ ተናገሩ፥ እንዲህም አድርጉ። ምሕረትን ለማያደርግ ምሕረት የሌለበት ፍርድ ይሆናልና፤ ምሕረትም በፍርድ ላይ ይመካል።
አሜን ፡፡
መልካም ዳግማይ ትንሣኤ!!


    በአለማችን በተለያዩ መስኮች እጅግ ከፍተኛ ተወዳጅነትና ተደናቂነትን ያተረፉ ግለሰቦችን ዝርዝር በየአመቱ ይፋ የሚያደርገው ዩጎቭ፣ ከሰሞኑም የ2018 ምርጦችን ይፋ ያደረገ ሲሆን የማይክሮሶፍቱ መስራች አሜሪካዊው ቢሊየነር ቢል ጌትስና ታዋቂዋ የሆሊውድ ተዋናይት አንጀሊና ጆሊ ቀዳሚነቱን ይዘዋል፡፡
ቢል ጌትስና አንጀሊና ጆሊ ላለፉት ሶስት ተከታታይ አመታት የአለማችን ቀዳሚዎቹ እጅግ ተወዳጅ ዝነኞች ሆነው መዝለቃቸውን የዘገበው ዘ ኢንዲፔንደንት፤ በዘንድሮው ዝርዝር ውስጥ በሁለቱም ጾታዎች 20 ሰዎች መካተታቸውንም አመልክቷል፡፡
ዩጎቭ ከ37 ሺህ በላይ ከሚሆኑ የ35 የአለማችን አገራት ዜጎች በድረገጽ በሰበሰበው የድምጽ አሰጣጥ መሰረት፤ በወንዶች ዘርፍ ከቢል ጌትስ ቀጥለው የአለማችን የአመቱ ተደናቂ የሆኑት የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ መሆናቸውንና ቻይናዊው የፊልም አክተር ጃኪ ቻን ሶስተኛ ደረጃን መያዙንም ጠቁሟል፡፡
የቢዝነስ ሰዎችና የስፖርቱ አለም ከዋክብት በበዙበት በዘንድሮው ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱት መካከል ዋረን በፌ፣ ክርስቲያኖ ሮናልዶ፣ ሜሲና ዴቪድ ቤካም ይገኙበታል ያለው ዘገባው፤በፖለቲካው መስክ ከተመረጡት መካከልም የቻይናው ፕሬዚዳንት ዢ ጂፒንግ፣ ዶናልድ ትራምፕ እና ቭላድሚር ፑቲን እንደሚገኙበት አስታውቋል፡፡
የመዝናኛው መስክ ዝነኞች በብዛት በተካተቱበት በሴቶች ዘርፍ በአንጻሩ፣ የሁለተኛነትን ደረጃ የያዙት የቀድሞዋ የአሜሪካ ቀዳማዊት እመቤት ሚሼል ኦባማ ሲሆኑ ታዋቂዋ የቶክሾው አቅራቢ ኦፕራ ዊንፍሬይ ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል፡፡
እስከ አስረኛ ባለው ደረጃ ውስጥ ከተካተቱት የአለማችን ሴቶች ውስጥ ቴለር ስዊፍት፣ ማዶና፣ ሂላሪ ክሊንተንና የጀርመን መራሂተ መንግስት አንጌላ መርኬል እንደሚገኙበትም ዘገባው ጠቁሟል፡፡

 የአሜሪካው ኩባንያ እጅግ ዘመናዊ እንደሆነ የተነገረለትን የጠፈር ላይ የቅንጦት ሆቴል በመክፈት፣ ለአንድ ምሽት 792 ሺህ ዶላር የመክፈል አቅም ላላቸው የናጠጡ ባለጸጎች አገልግሎት ሊሰጥ በዝግጅት ላይ  እንደሚገኝ ማስታወቁ ተዘግቧል፡፡
ተቀማጭነቱን በሂውስተን ያደረገው ኦሪዮን ስፓን የተባለ ኩባንያ ከሶስት አመታት በኋላ በሚጀምረው በዚህ የቅንጦት የጠፈር ሆቴል ለመጀመሪያ ጊዜ አራት ደንበኞችን ለማስተናገድ ማሰቡን የዘገበው ብሉምበርግ፤ ደንበኞቹ በህዋው ሆቴል ለሚኖራቸው የ12 ቀናት ቆይታ እያንዳንዳቸው 9.5 ሚሊዮን ዶላር እንደሚከፍሉ አመልክቷል፡፡
ኩባንያው በሁለት የበረራ ባለሙያዎች በምትመራዋና 35 ጫማ በ14 ጫማ ስፋት ባላት መንኮራኩር ላይ በሚከፍተው በዚህ የጠፈር ላይ ዘመናዊ ሆቴል፤ የመክፈል አቅም ላላቸው ደንበኞች ከምድር በ200 ማይል ርቀት ላይ ከመሬት ስበት ውጭ ሆነው ለቀናት ሙሉ መስተንግዶ የሚያገኙበትን ዕድል ለመፍጠር ዝግጅቱን እያጧጧፈ እንደሚገኝ አስታውቋል፡፡
በአለማችን የጠፈር ቱሪዝም ታሪክ በግላቸው ከፍተኛ ገንዘብ በመክፈል ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ጠፈር የተጓዙት አሜሪካዊው ባለሃብት ዴኒስ ቲቶ እንደነበሩ ያስታወሰው ዘገባው፤ ግለሰቡ በ2001 ወደ አለማቀፉ የጠፈር ማዕከል ላደረጉት ጉዞ 20 ሚሊዮን ዶላር ያህል መክፈላቸውንም ጠቁሟል፡፡

  በአለማችን 22 ሺ ያህል ሰዎች የሞት ፍርድ ይጠብቃቸዋል

    አለማቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ተቋም አምነስቲ ኢንተርናሽናል፤ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን ሰዎች በሞት በመቅጣትና በመግደል የምትታወቀው ቻይና፤ አሁንም ከአለማችን አገራት ቀዳሚነቱን መያዟን ከትናንት በስቲያ ይፋ ባደረገው አመታዊ ሪፖርቱ አስታውቋል፡፡
ቻይና ባለፈው የፈረንጆች አመት 2017 በሺህዎች በሚቆጠሩ ሰዎች ላይ የሞት ፍርድ ቅጣት ማስተላለፏን የጠቆመው የተቋሙ ሪፖርት፤ በአመቱ የገደለቻቸው ሰዎች ትክክለኛ ቁጥር ባይታወቅም በተቀረው አለም አገራት የተፈጸሙ ግድያዎች ተደምረው የቻይናን እንደማይደርሱ አመልክቷል፡፡
በአመቱ በርካታ ሰዎችን በሞት በመቅጣት በሪፖርቱ ከተጠቀሱ አገራት መካከል ኢራን፣ ሳኡዲ አረቢያ፣ ኢራቅና ፓኪስታን የሚገኙበት ሲሆን  በእነዚህ አገራት በድምሩ ከ830 በላይ ሰዎች በሞት መቀጣታቸውንም አክሎ ገልጧል፡፡
በአመቱ የሞት ቅጣት ፍርድና ግድያ በመላወ ዓለም በተወሰነ ደረጃ መቀነስ ማሳየቱን ያስታወቀው የአምነስቲ ሪፖርት፤ በ2017 የፈረንጆች አመት ቻይናን ሳይጨምር በአለማችን 23 አገራት የሞት ቅጣት የተፈረደባቸው 993 ሰዎች መገደላቸውን አመልክቷል። በአለማችን በሚገኙ 53 አገራት፣ ምንም እንኳን በሁሉም ላይ ተፈጻሚ ባይደረግም በ2ሺህ 591 ሰዎች ላይ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸዋል ያለው ሪፖርቱ፤ በመላው አለም 22 ሺህ ያህል ሰዎች የሞት ፍርድ ይፈረድባቸዋል ተብሎ እንደሚጠበቅም አስታውቋል፡፡
ከሰሃራ በታች ባሉ አገራት ተስፋ ሰጪ ነገር መታየቱንና 20 ያህል የአካባቢው አገራት የሞት ፍርድ እንዲቀር መወሰናቸውን የጠቆመው ሪፖርቱ፤ አንዳንድ አገራት በአንጻሩ ከልክለውት የነበረውን የሞት ፍርድ ቅጣት በ2017 እንደገና ተግባራዊ ማድረግ መጀመራቸውን ጠቅሶ፤ከእነዚህም መካከል ባህሬን፣ ዮርዳኖስ፣ ኩዌትና የተባበሩት አረብ ኤሜሬትስ እንደሚገኙበት አስረድቷል፡፡

   የአለም የጤና ድርጅት ባለፈው ቅዳሜ በሶርያዋ ዱማ ከተማ በተፈጸመው ጥቃት የኬሚካል ጦር መሳሪያ ሰለባ በመሆን ለህመም የተዳረጉ የአገሪቱ ዜጎች ቁጥር 500 ያህል መድረሱን ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
ድርጅቱ ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ፤ ህጻናትን ጨምሮ ለህመም የተዳረጉት 500 ያህል ሶርያውያን የመርዛማ ኬሚካል ጦር መሳሪያ ጥቃት እንደተፈጸመባቸው የሚጠቁሙ የመተንፈሻ አካላትና የአእምሮ ስርዓት ችግር ምልክቶች እንዳሳዩ በሃኪሞች ተረጋግጧል ማለቱን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
የበሽር አልአሳድ መንግስት 70 ሰዎች ያህል ለህልፈተ ህይወት ተዳርገውበታል የተባለውን የምስራቃዊ ጉታ የኬሚካል ጦር መሳሪያ ጥቃት አለመፈጸሙን በመግለጽ፤ አለማቀፍ ተቋማት ጉዳዩን እንዲያጣሩ የጠየቀ ሲሆን በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሶርያ አምባሳደር ሁሳም ኢዲን አላም በበኩላቸው፤ የአለም የጤና ድርጅት ይፋ ያደረገውን መረጃ፣ መሰረተ ቢስ ውንጀላ ነው ሲሉ ማጣጣላቸውን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
በሶርያ የኬሚካል ጦር መሳሪያ ጥቃት ሰለቦችን የማከምና የመንከባከብ ተልዕኮ የተሰጣቸው 800 የአገሪቱ የጤና ሰራተኞችን ማሰልጠኑን የጠቆመው የአለም የጤና ድርጅት፤ በምስራቃዊ ጉታ ጥቃት ለደረሰባቸው ለእነዚህ ዜጎች አፋጣኝ የህክምና እርዳታ ለመስጠት እንዲቻል የበሽር አል አሳድ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርግ መጠየቁንም ዘገባው አመልክቷል፡፡ የበሽር አልአሳድ መንግስት የኬሚካል ጦር መሳሪያ ጥቃቱን አልፈጸምኩም ቢልም የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማርኮን በበኩላቸው፤ ጥቃቱን መፈጸሙን የሚያረጋግጥ ተጨባጭ መረጃ ማግኘታቸውን ከትናንት በስቲያ ገልጸዋል፡፡
ለጥቃቱ ሶርያንና ሩስያን ተጠያቂ ያደረጉት አሜሪካና እንግሊዝን ጨምሮ የተለያዩ የአውሮፓ አገራት መንግስታት፤ በመርዛማ ጋዝ ጥቃቱ ብዙዎችን ሰለባ አድርገዋል ባሏቸው የሶርያው ፕሬዚዳንት በሽር አል አሳድ ላይ ወታደራዊ እርምጃ መውሰድ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ በጋራና በተናጠል እየተወያዩ እንደሆነና የሩስያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ ወታደራዊ እርምጃው እንዳይወሰድ ማስጠንቃቃቸው ተዘግቧል፡፡

ጥንት በቀዝቃዛው ጦርነት ዘመን አንድ ምስኪን አሜሪካዊ፤ በአሜሪካኑ ሁዋይት ሐውስ ፊት ለፊት፣ ሣር ሲግጥ ይታያል፡፡ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሰገነታቸው ላይ ቆመው ይህ ዜጋ ሳር ሲግጥ በማየታቸው እጅግ ተደንቀው ያስጠሩታል፡፡
ፕሬዚዳንት፤
“ምን ሆነህ ነው ሳር የምትግጠው?”
ምስኪኑ ዜጋም፤
“ርቦኝ፡፡ ጠኔ ሊገለኝ ሲሆን ሳርም ቢሆን ልቅመስ ብዬ ነው!”
ፕሬዚዳንት፤
“በል በቃህ፡፡ ለአምስት ዓመት በቀን ሶስት ጊዜ ማክዶናልድ (ሀምበርገር) በእኔ ሂሳብ ትበላለህ”፤ ግን ሥራ ፈልግ” ብለው አሰናበቱት፡፡ ተደስቶ ጮቤ እየረገጠ ሄደ፡፡
አምስት ዓመት በላ፡፡ አምስት ዓመት ጠገበ፡፡ ሥራ ግን አሁንም አላገኘም!
ስለዚህ ወደ ሩሲያ ሄደ፡፡ ሩሲያ ጥቂት እንደቆየ መራብ ጀመረ፡፡ ረሀቡን ለማስታገስ ወደ ዋናው የመንግሥት መናኸሪያ ወደ ክሬምሊን ሄደ፡፡ ከዚያም ፊት ለፊት ያገኘውን ሣር መጋጥ ጀመረ፡፡ የሩሲያው ፕሬዚዳንት ብሬዤኔቭ አዩት፡፡ ነገሩ ገርሟቸው አስጠሩት፡፡ በአጃቢ ገብቶ ፊታቸው ቀረበ፡፡ ብሬዥኔቭም፤
“ምን ሆነህ ነው እንዲህ እየተስገበገብክ ሳር የምትግጠው?” ሲሉ ጠየቁት፡፡
ምስኪኑ አሜሪካዊም፤
“ርሃብ! ጠኔ ሊገለኝ ነው ክቡር ፕሬዚዳንት!”
ፕሬዚዳንቱ ትንሽ አቅማሙና፤
“ታዲያ ለነገዬ አትችልም? ፕላንድ ኢኮኖሚ አታውቅም? በአንድ ቀን ግጠህ ልትጨርሰው ነው?” ብለው ኢኮኖሚያዊ ግሳፄ ሰጡት!!
*   *   *
አሜሪካኖች ሥራ ከመስጠት ይልቅ፤ ብር መስጠት ወደዱ፡፡ ሩሲያውያን በባዶ ሆድህ ቁጠባን ዕወቅ አሉ፡፡ ዓለም እንደዚያ ነበረች፡፡ ከዚያ ይሰውረን!
ለያዥ ለገራዥ ያስቸገረው የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ፤ ዛሬም በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንደሆነ አለ! የዓለም ባንክና የዓም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) ዘገባዎች፤ (የአየለ አይኤምኤፍን ነብስ ይማር!) በኢትዮጵያ ኑሮና ካዝና አንፃር፡-
“ላም አለኝ በሰማይ
ወተቷንም አላይ” ናቸው፡፡ እንጂ እንደ  ካፒታሊስቶቹ ምኞትማ፡-
“ላም አለኝ በሰማይ
ወተቷ እሚከራይ!” በሆነ ነበር!
ከሁሉም ያውጣን!
“ገንዘቤን የወሰደ ሰው፣ ወሰደ እንበል ከንቱ ነገር የእኔም የሱም የዚያም ነበር
ግና ስሜን የሰረቀኝ የማያከብረውን ወስዶ፣ እኔን በግልፅ አደኸየኝ” (ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን)
ከማለት ሌላ ምን አቅም አለን፡፡
ካርል ማርክስ እንደሚለንም፤
“ፖለቲካ የኢኮኖሚ ጥርቅም መልክ ነው” (Politics is the concentrated form of economics)
ይህ እንግዲህ በሀገራችን ተሾመም፣ ተመረጠም፣ መሪ የሆነ ሰው፤ የፖለቲካም የኢኮኖሚም የአደራ ዕዳ እንዳለበት ነው፡፡ የህዝቡ ኑሮ እጅግ ጠያቂ ነው፡፡ ማንንም አይምርም! ይፈታተናል፡፡ ብልህ መሪ፤ አስተዋይ፣ ሆደ - ሰፊ፣ ትዕግሥቱን በብዛት የሰጣቸውን ባለ ራዕይ ጠቢባን የኢኮኖሚ ባለሙያዎችን በዙሪያው ሰብስቦ፡-
“ነገርን ከሥሩ
ውሃን ከጥሩ”
ማጤን ይጠበቅበታል!
“ጣሊያን ሊማሊሞን በመድፍ ሲደበድበው አደረ” ቢሉት፤
“ተወው ይበለው! እሱም መገተሩን አብዝቶት ነበር” አለ አሉ የጎንደር ሰው፡፡ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ግን በመድፍም ቢመታ ውልፊት አይልም! እንኳንስ በአንድ ጀምበር በአያሌ ጀምበሮችም የማይነቀነቅ ስለሆነ፣ “እንኳን ተለያይተን አንድ ሆነንም አስቸጋሪ ነው” ማለት ትክክለኛ አቅጣጫ ነው!
ተባብረን የኢኮኖሚያችንን ነገር ምን እናድርገው? እንባባል!
የቀድሞ፣ ቀድሞ መሪያችንን ራዕይ ብቻ የሙጥኝ በማለት አንወጣውም! ከአዳጊው ሁኔታ ጋር ምን ምን የኢኮኖሚ መንገድ እንቀይስ ካልተባባልን፣ የተሾመን የሚሽር፣ የመጣን የሚያወርድ አደጋ ፊታችን ላይ ተደቅኗል! እንደ ወትሮው፣
“ብቆጣም እመታሻለሁ፤ ብትቆጪም እመታሻለሁ” ዓይነት ዲሞክራሲ ዛሬ ወንዝ አያሻግርም! ደጋግመን “ፖለቲካው የኢኮኖሚው ጥርቅም መልክ ነው!” የሚለውን ጥልቅ አስተሳሰብ፤ በጥልቅ ግምገማም ቢሆን እንመርምረው!
ለክርስትና ሃይማኖት ተከታዮች
መልካም የዳግማይ ትንሣዔ በዓል!

 ትዝ ይለኛል የዛሬ አስራ አራት አመት ነው፡፡ ከባለቤቴ ጋር አብረን ለመኖር ስወስን አንድ የቅርብ ወዳጄን ላገባ ነው ብዬ አማከርኩት፡፡ “እሱም ትዳር ጥሩ ነው፤ አግባ ግን ሪሞት ኮንትሮልህን አሳልፈህ እንዳትሰጥ” አለኝ፡፡ የመጀመሪያዎቹን ስድስት ወራት ሪሞት ኮንትሮሉን ላለመስጠት ብዙ ታገልኩ። ግን አልቻልኩም ፍቅር አሸነፈኝ፡፡ እናም ሪሞት ኮንትሮሉን አሳልፌ ሰጠሁ፡፡
ይህን በማድረጌ ግን ሦስት በዚህ ዓለም ላይ ካሉ ጥሩ ነገሮች ሁሉ አብልጬ እምወዳቸው ውብ ልጆች አተረፍኩ፡፡
ታዲያ ሁሌ የቴሌቪዥኔን ሪሞት ኮንትሮል ባየሁ ቁጥር፣ ያ ወዳጄ ትዝ ይለኛል፡፡ አንዳንዴ ደግሞ አስባለሁ፤ አሁን እሳት ቢነሳ እማድነው ሪሞት ኮንትሮሉን ነው ወይስ ቴሌቪዥኑን? የሚቀለው ሪሞት ኮንትሮሉን ብድግ አድርጎ መሮጥ ነው፤ ግን ቴሌቪዥኑ ከሌለ ሪሞት ኮንትሮሉ ብቻውን ምን ይሰራል? ቢከብድም ቴሌቪዥኑን ማዳን ግን  ይጠቅማል፤ ምክንያቱም ቴሌቪዥኑ ከዳነ በኋላ ሪሞት ኮንትሮሉ በቀላሉ ስለሚገኝ፤ ባይገኝም  ቴሌቪዥኑ ምቾት ይቀንሳል እንጂ ያለ ሪሞት ኮንትሮል ማሳየት ስለሚችል! አሁን ሀገራችንን  እንደ ቴሌቪዥን፣ ስልጣንን ደግሞ እንደ ሪሞት ኮንትሮል እንይ፡፡
እሳት ሀገራችን ላይ ተነስቷል፡፡ እምናተርፈው ሪሞቱን ነው ወይስ ቴሌቪዥኑን? 180 አሁን ይህ ቁጥር ለሐገራችን ብዛትን መግለጫ ተራ ቁጥር አይደለም፡፡ ይህ ቁጥር ቀጣዩን የኢትዮጵያን እጣ ፈንታ የሚወስን ቁጥር ነው፡፡ እናንተ አንድ መቶ ሰማንያ ሰዎች!! ምናልባትም በታሪካችን ለመጀመሪያ ጊዜ ሀገራችሁ እጃችሁ ላይ ወድቃለች፡፡
ይህ ወቅት እንደ ሌላው ጊዜ እጅ አውጥታችሁና አጨብጭባችሁ የምትለዩት ወቅት አይደለም!! ይህ ወቅት እድሜ ልካችሁን በፀፀት ወይም በእርካታ የሚከተላችሁ ታሪካዊ ወቅት ነው!! እናም ተተኪውን ጠቅላይ ሚኒስትራችንን ስትመርጡልን.........ስለ ብሄር ሳታስቡ.......በተፅእኖ ሳትረቱ.........ስለ ምቾታችሁ ሳትጨነቁ.......በሆዳችሁም በልባችሁም ሳይሆን በጭንቅላታችሁ ብቻ አስባችሁ........... ለወከላችሁ ብሔር ብቻ ሳይሆን ሳይፈልጉ እጃችሁ ስር ለወደቁ መላ ኢትዮጵያውያን ጭምር ተጨንቃችሁ፣ ይህቺን አገር ከገባችበት አዘቅት የሚያወጣት፤ ኢትዮጵያውያንን  ከዞረብን የዘረኝነት አባዜ የሚያላቅቀን፤ እያደር በጥልቀት ከምንሰምጥበት ያስተሣሠብ ድህነት የሚያድነን፤ ከዘወትር ተመፅዋችነት የምንገላገልበትን አቅጣጫ የሚያሣየን፤ መሪ ምረጡልን!ሪሞት ኮንትሮሉን ሳይሆን ቴሌቪዥኑን አድኑልን፡፡ ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ህዝቦቿን ይባርክ፡፡
(ከቴዎድሮስ ተሾመ ፌስቡክ)

 ትዝ ይለኛል የዛሬ አስራ አራት አመት ነው፡፡ ከባለቤቴ ጋር አብረን ለመኖር ስወስን አንድ የቅርብ ወዳጄን ላገባ ነው ብዬ አማከርኩት፡፡ “እሱም ትዳር ጥሩ ነው፤ አግባ ግን ሪሞት ኮንትሮልህን አሳልፈህ እንዳትሰጥ” አለኝ፡፡ የመጀመሪያዎቹን ስድስት ወራት ሪሞት ኮንትሮሉን ላለመስጠት ብዙ ታገልኩ። ግን አልቻልኩም ፍቅር አሸነፈኝ፡፡ እናም ሪሞት ኮንትሮሉን አሳልፌ ሰጠሁ፡፡
ይህን በማድረጌ ግን ሦስት በዚህ ዓለም ላይ ካሉ ጥሩ ነገሮች ሁሉ አብልጬ እምወዳቸው ውብ ልጆች አተረፍኩ፡፡
ታዲያ ሁሌ የቴሌቪዥኔን ሪሞት ኮንትሮል ባየሁ ቁጥር፣ ያ ወዳጄ ትዝ ይለኛል፡፡ አንዳንዴ ደግሞ አስባለሁ፤ አሁን እሳት ቢነሳ እማድነው ሪሞት ኮንትሮሉን ነው ወይስ ቴሌቪዥኑን? የሚቀለው ሪሞት ኮንትሮሉን ብድግ አድርጎ መሮጥ ነው፤ ግን ቴሌቪዥኑ ከሌለ ሪሞት ኮንትሮሉ ብቻውን ምን ይሰራል? ቢከብድም ቴሌቪዥኑን ማዳን ግን  ይጠቅማል፤ ምክንያቱም ቴሌቪዥኑ ከዳነ በኋላ ሪሞት ኮንትሮሉ በቀላሉ ስለሚገኝ፤ ባይገኝም  ቴሌቪዥኑ ምቾት ይቀንሳል እንጂ ያለ ሪሞት ኮንትሮል ማሳየት ስለሚችል! አሁን ሀገራችንን  እንደ ቴሌቪዥን፣ ስልጣንን ደግሞ እንደ ሪሞት ኮንትሮል እንይ፡፡
እሳት ሀገራችን ላይ ተነስቷል፡፡ እምናተርፈው ሪሞቱን ነው ወይስ ቴሌቪዥኑን? 180 አሁን ይህ ቁጥር ለሐገራችን ብዛትን መግለጫ ተራ ቁጥር አይደለም፡፡ ይህ ቁጥር ቀጣዩን የኢትዮጵያን እጣ ፈንታ የሚወስን ቁጥር ነው፡፡ እናንተ አንድ መቶ ሰማንያ ሰዎች!! ምናልባትም በታሪካችን ለመጀመሪያ ጊዜ ሀገራችሁ እጃችሁ ላይ ወድቃለች፡፡
ይህ ወቅት እንደ ሌላው ጊዜ እጅ አውጥታችሁና አጨብጭባችሁ የምትለዩት ወቅት አይደለም!! ይህ ወቅት እድሜ ልካችሁን በፀፀት ወይም በእርካታ የሚከተላችሁ ታሪካዊ ወቅት ነው!! እናም ተተኪውን ጠቅላይ ሚኒስትራችንን ስትመርጡልን.........ስለ ብሄር ሳታስቡ.......በተፅእኖ ሳትረቱ.........ስለ ምቾታችሁ ሳትጨነቁ.......በሆዳችሁም በልባችሁም ሳይሆን በጭንቅላታችሁ ብቻ አስባችሁ........... ለወከላችሁ ብሔር ብቻ ሳይሆን ሳይፈልጉ እጃችሁ ስር ለወደቁ መላ ኢትዮጵያውያን ጭምር ተጨንቃችሁ፣ ይህቺን አገር ከገባችበት አዘቅት የሚያወጣት፤ ኢትዮጵያውያንን  ከዞረብን የዘረኝነት አባዜ የሚያላቅቀን፤ እያደር በጥልቀት ከምንሰምጥበት ያስተሣሠብ ድህነት የሚያድነን፤ ከዘወትር ተመፅዋችነት የምንገላገልበትን አቅጣጫ የሚያሣየን፤ መሪ ምረጡልን!ሪሞት ኮንትሮሉን ሳይሆን ቴሌቪዥኑን አድኑልን፡፡ ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ህዝቦቿን ይባርክ፡፡
(ከቴዎድሮስ ተሾመ ፌስቡክ)

 “--አጎዛውን ግድግዳ ላይ ሰቅለው፣ ለጌጥና ለዓይን ማረፊያ ያደርጉታል፡፡ ከዚያ ያወርዱና አንጥፈው ይተኙበታል፡፡ ሲተኙ ደግሞ ያሸትቱታል፡፡ እነዚህ የውበት ልምምዶች ሁለት አይነት ነገር አላቸው፤ ተግባራዊም ውበታዊም፡፡--”

    ተወልዶ ያደገው በጎጃም ገጠር ቢሆንም ያደገውና የተማረው በባህርዳር ከተማ ነው - ሰዓሊ እያዩ ገነት፡፡ የመጀመሪያ ድግሪውን ከባህርዳር ዩኒቨርሲቲ በኢኮኖሚክስ ቢያገኝም የነፍሴ ጥሪ እንዳልሆነ ስገነዘብ፣የወርልድ ቪዥን ሥራዬን ጥዬ፣ ወደ አዲስ አበባ መጣሁና የስዕል ት/ቤት ገባሁ ይላል፡፡ በትምህርቴ “ሰቅዬ” በመቅረት በስዕል    ት/ቤት ውስጥ የተወሰነ አበርክቶ ይኖረኛል የሚል እምነት ነበረኝ የሚለው ሰዓሊው፤ ነገር ግን በተለያዩ ምክንያቶች ሳይሳካ ቀረና የሀይስኩል ተማሪዎችን በራሴ ተነሳሽነት፣ ስዕል ማስተማር ጀመርኩኝ ብሏል፡፡ በፋይን አርት ዲግሪውን ከአገኘ በኋላስ? የጥበብ ጉዞው ምን ይመስላል? ወደ ባህርዳር ይዤው ሄድኩ ስለሚለው ህልሙ ያወጋናል፡፡ ስዕል እንጀራ አይሆንም በሚል የሚንጸባረቀውን  አመለካከትም ይሞግታል። ስለ ምዕራቡ ዓለም የሥነ ጥበብ ፍልስፍና፣ “ነቁጥ” በሚል ስያሜ በጉራማይሌ የሥነጥበብ ጋለሪ ለዕይታ ስላቀረበው አውደ ርዕይ ያብራራል፡፡ ሰዓሊው በቅርቡ በግብጽና በኢኳዶር በሚካሄድ የሥነ ጥበብ ሲምፖዚየም ላይ እንደሚሳተፍም ይገልጻል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ሰዓሊውን በጥበብ ህይወቱ ዙሪያ አነጋግራዋለች፡፡ እነሆ፡-  


   ስሜትህ ለስነ-ጥበብ እያደላ እንዴት ኢኮኖሚክስ ለመማር ዩኒቨርሲቲ ገባህ?
“ብልጥ ልጅ እየበላ ያለቅሳል” ይላሉ አበው። በውስጤ የስነ-ጥበብ ፍቅር ቢኖረኝም አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተገብቶ መማር እንደሚቻል የነገረኝ ወይም መንገዱን ያሳየኝ አልነበረም፡፡ ብቻ ባህርዳር ላይ ዘውዱ ባይሌ የሚባል ሰዓሊ ነበር (ነፍሱን ይማርና) ጋለሪ ከፍቶ የማስታወቂያ ስራ ሲሰራ እያየሁ፣ እሱን ነበር መሆን የምፈልገው፡፡ ነገር ግን በወቅቱ የትምህርት ውጤቴ ጥሩ ስለነበር ካሉት ትምህርቶች የተሻለ ነው ብዬ ያመንኩትን የኢኮኖሚክስ ትምህርት ልማር ቻልኩኝ፡፡
በተማርከው ትምህርት ሰራህበት ታዲያ? ከዚያስ እንዴት ወደ አለ የስነ ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት ገባህ?
በኋላ ላይ ጥሪሽ እንዳልሆነ ሲገባሽ ሁሉም ነገር ትግልና ፈተና ይሆንብሻል፡፡ ላልተፈጠርንበት አላማ ምናልባት ችለን በእጃችን ልንሄድ እንችላለን ግን እጅ እንደ እግር እንደማይሆን የተረዳን ሰዓት፣ በእግር መሄድ ስንሞክርና በጣም ምቹ መሆኑን ስንረዳ በእጃችን የሄድንበትን ጊዜ እንፀፀትበታለን። ምን ለማለት ነው… ለአፍንጫም ለአይንም አሁን ካለበት የተሻለ ቦታ የለም። በኢኮኖሚክሱ ሰርተህበታል ወይ ላልሺኝ፤ እርግጥ ነው ወርልድ ቪዥን ገብቼ ስራ ጀምሬ ነበር፡፡ ነገር ግን ለዚያ ቦታና ስራ የተፈጠርኩ አለመሆኔ ሲገባኝና የነፍሴ ጥሪ አርት እንደሆነ ስረዳ፣ ወደ አዲስ አበባ መጥቼ አርት ት/ቤት ገባሁ፡፡ በወቅቱ ቤተሰቤም እንጀራ ትተህ ሄደህ እንጀራ አይወጣልህም ብለውኝ ነበር፤ ደስተኞችም አልነበሩም፡፡ እኔ ግን ትዝ ይለኛል፣ ወደ አዲስ አበባ ስመጣ በኪሴ የነበረው 300 ብር ብቻ ነበር። ጫማ ጠርጌም ቢሆን የተጠራሁበትን ዓላማ አሳካለሁ የሚለውን ህልም ይዤ ነው የወጣሁት። ከዚያ አራት አመት በአርት ስኩል ትምህርቴን ስከታተል ቆይቼ፣ በፋይን አርት ዲግሪዬን አገኘሁ፡፡
በስዕል ት/ቤት በነበረህ ቆይታህ ከመደበኛው ትምህርት ውጭ በራስህ ላይ የጨመርከውን ነገር ንገረኝ…?
እንደኔ አመለካከት ትምህርት አንቺን አይፈጥርሽም ግን የተፈጠረውን አቅምሽን ቅርፅ በመስጠትና አቅጣጫ በማስያዝ ከፍተኛ እገዛ ያደርግልሻል፡፡ እኔ በተለይ ከመምህራኖቼ በጣም የሚያስገርሙ አቅሞችን አግኝቻለሁ፡፡ እነ መዝገቡ ተሰማ፣ ታደሰ መስፍን፣ ጌታሁን አሰፋ፣ በቀለ መኮንንና ሌሎችም አመለካከትን ሊቀይሩ ከሚችሉ ሰዎች ጋር የመገናኘት ዕድል ማግኘትሽ ያለሽን ነገር ጥልቀት ይጨምርልሻል፡፡ በዚህ ምክንያት ለሙያው ያለኝ ጥማት ጨርሶ ነደደ፡፡ መጀመሪያም ፓሺን ነበረኝ፤ ትምህርቱ ደግሞ የበለጠ ፍቅርና ፍላጎቱን አቀጣጠለልኝ፡፡ እርግጥ ነው መጀመሪያ ላይ የሚያሳጣሽ ነፃነት አለ…፡፡
ምን አይነት ነፃነት ነው የሚያሳጣው?
የምንማርበት ሥርዓተ ትምህርት የተቀረፀው በምዕራቡ አስተሳሰብ ላይ ማዕከል አድርጎ በመሆኑና የአገራችንን ነባራዊ ሁኔታ ከግንዛቤ ውስጥ ስለማያስገባ በጣም ገዳቢ ነው፡፡ ነገር ግን አንቺ ብልህ ከሆንሽ ያንን ትምህርት ከራስሽ ሁኔታ አንፃር እየቃኘሽ መጠቀም ትችያለሽ፡፡ እኔም በት/ቤት ቆይታዬ ይህንን ሳደርግ ነው የቆሁት፡፡ ከዚያ በኋላ በነበረኝ ፍቅር… በውጤቴ ምክንያት እዚያው ት/ቤት በመምህርነት እቆያለሁ የሚል እምነት ነበረኝ፡፡ እንደው እዚያው ጨርሶ መቅረትም ባይሆን እንኳን የተወሰነ አበርክቶ ይኖረኛል የሚል ሀሳብ ነበረኝ፡፡ ነገር ግን በተለያዩ ምክንያቶች ሳይሳካ ቀረና የሀይስኩል ተማሪዎችን በራሴ ተነሳሽነት፣ ደስ ብሎኝ ስዕል ማስተማር ጀመርኩኝ። ይህን እያደረግኩኝ ዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ አርኪቴክቸር ዲፓርትመንት የማስተማር ዕድል አገኘሁ፡፡ እዛም ለአንድ ዓመት ያህል ሰራሁ፡፡
ብዙ የስዕል አውደ ርዕዮች ላይም ተሳትፈሃል…?
አውደ ርዕዮችን--- በአሊያንስ ኢትዮ ፍራንሴዝ፣ በጎተ ኢንስቲትዩት፣ በአሜሪካ ኤምባሲና በሌሎች ቦታዎች በቡድን አቅርቤአለሁ፡፡ ይህንን ሳደርግ ግን የቀደሙ አርቲስቶች የሚሰሩትን እንደምደግም እንጂ አዲስ ነገር እንደማልሰራ ተረዳሁ፡፡ ከዚያ አንድ ህልም ይዤ ወደ ባህርዳር ሄድኩኝ፡፡ እንደምታውቂው አለ የስነ-ጥበብና የዲዛይን ት/ቤት 50 ዓመት ሞልቶታል፡፡ ከዚያ የሚወጡ አብዛኞቹ ሰዓሊዎች እዚህ አዲስ አበባ ነው የሚሆኑት። ምክንያቱም አዲስ አበባ የብዙ ኤምባሲዎች፣ የዲፕሎማቶች መቀመጫ በመሆኗ ገበያው ያለው እዚሁ ስለሆነ ነው፡፡ ወደ ክልል አይወጡም፡፡ ክልል ላይ ደግሞ በተደራጀ መልኩ የሚካሄድ የአርት እንቅስቃሴ የለም፡፡ እኔ ደግሞ ባህርዳር ያደግኩባት ከተማ ናት፡፡ ቤተሰቦቼም ያሉት እዚያው ናቸው፡፡ ስለዚህ ባህርዳር የቱሪስት ከተማ በመሆኗ አማራጭ የስነ ጥበብ ከተማ (Alternative Art corner) የማድረግ ህልም ይዤ ወደ ከተማዋ ተመለስኩኝ። እድለኛ ነኝ፤ ባለቤቴም ስራዋን ትታና ህልሜን ተከትላ አብራኝ መጣች፡፡ ከዚያም አንድ ት/ቤት ውስጥ ማስተማር ጀመርኩኝ፡፡
በባህርዳር ዩኒቨርሲቲ የአርኪቴክቸር ዲፓርትመንት የአርት ኮርሶችን ትሰጣለህ አይደል?
ትክክል ነው፤ አስተምራለሁ፡፡ ቅድም ያልኩሽ ት/ቤት እያስተማርኩ እያለሁ አቫንቲ ብሉናይል ሆቴል፣ አሁን ብሉናይል ሪዞርት ሆቴል ሆኖ የተቀየረው አንድ ነገር አደረገልኝ፡፡ አንድ ቀን፤ “ፈጣሪ እባክህ ያለምኩትን አሳካልኝ” ብዬ ፀሎት አደረግሁኝ፡፡ እኔ ህልሜ ታዋቂ ለመሆን አይደለም፤ ብዙ ብር ለመሰብሰብ አይደለም፤ ግን ይህ ህልሜ የእውነት መስመር እንዲይዝ እፈልጋለሁ” አልኩና ፀልዬ ወደ ነገርኩሽ ሆቴል ሄድኩኝ፡፡ ሀላፊው ሚስተር ስቴቨን ይባላል፤ አገኘሁት፡፡ በሚገርም ሁኔታ ሆቴሉ መቶ ሺህ ብር ስፖንሰር አድርጎኝ፣ 50 ያህል ስራዎችን ማቅረብ ቻልኩኝ፡፡ ካቀረብኳቸው ስራዎች ውስጥ እድለኛ ሆኜ፣ ከ20-30 ያህሉ ስዕሎች ከ2-7 ሺ ብር በሚደርስ ዋጋ ተሸጡ፡፡ በዚህ ውጤት ህይወቴን፣ ከቤተሰቤም ጋር ያለውን ነገር አስተካከልኩኝ፡፡ በርካታ ጉዳዮችን ከወንኩኝ፡፡
በዚህ መሃል የቀድሞው የባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ባይሌ ዳምጤ፣ በስዕል ኤግዚቢሽኑ ስነ-ስርዓት ላይ ከባለቤታቸው ጋር ታድመው ነበርና፣ “ከተማችን እንዲህ አይነት ልጅ አለን እንዴ? ለአርኪቴክቸር ዲፓርትመንት ብዙ ጊዜ ማስታወቂያ አውጥተን አላገኘንም” ብለው ሪኮመንድ አደረጉኝ፡፡ ቅድም እንዳልሺው በዩኒቨርሲቲው ማስተማር ጀመርኩኝ ማለት ነው። ለሙያው ካለኝ ፍቅር የተነሳ ተማሪም እያለሁ፣ ሁለት ክረምቶች 80 ያህል ወጣቶችን በስዕል ትምህርት በበጎ ፈቃደኝነት አሰልጥኛለሁ፡፡  ከነዚህ መካከል ከ10 በላይ ሰልጣኞች፣ አለ የስነ ጥበብ ዲዛይን ትምህርት ቤት ለመግባት ችለዋል፡፡ ይሄም እድለኛ ነኝ ያሰኘኛል፡፡ አሁን ልጆቹ በጥሩ ሁኔታ እየተንቀሳቀሱ ነው፡፡ በዚህ በጣም ደስተኛ ነኝ፡፡
እኛ አገር ላይ ስዕል እንጀራ አይሆንም የሚለው አመለካከት በስፋት ይንፀባረቃል፡፡ አንተስ ይህን አመለካከት  ትጋራዋለህ?
ምን መሰለሽ… እንጀራ ይሆናል ብለሽ፣ እንጀራ እንጀራውን እያሰብሽ ከገባሽበት እንጀራ አይሆንም። ነገር ግን ሙያውን የእውነት ወደሺው፣ ራስሽን ሰጥተሸ ከልብሽ ስትሰሪ እንጀራ መሆን ይጀምራል። ስለዚህ ሙያችንን ወድደነው፣ በፍቅርና በትጋት ነወይ የምንሰራው? የሚለው ጥያቄ መመለስ አለበት፡፡ ሙያችንን ወድደን ራሳችንን ሆነን ሥንሰራ፣ የማንንም አንገለብጥም፡፡ ስለዚህ ትኩረት እንስባለን፡፡ አሁን ሰው ለአርቱ ያለው አመለካከት እየተቀየረና አይኑ እየተከፈተ ነው። እኔ ለምሳሌ ሙያዬ በአንድ አቅጣጫ ብቻ ገቢ እንዲያመጣልኝ አልፈልግም፡፡ የህትመት ስራዎች ሰርቻለሁ፣ ዲዛይኖች ሰርቻለሁ፡፡ ጨጨሆ የባህል ምግብ አዳራሽን ካየሺው፣ የባህርዳሩንም የአዲስ አበባውንም ስዕሎች የሰራሁት እኔ ነኝ፡፡ አሁን ይህ ስራ አድካሚና እልህ አስጨራሽ ነው፡፡ 20 ሜትር በ7 ሜትር ስዕል መሳል ከባድ ነው፡፡ ከዚያ ይልቅ ትንንሽ ብዙ ስዕሎችን መስራት ይቀላል፡፡ እኔ የማስበው ያሉኝን ነገሮች ተጠቅሜ፣ ሙያዬን ወደ ገንዘብ መቀየርና ከአንድ አቅጣጫ ጠባቂነት ራሴን ማውጣት ነው፡፡ በዚህ በኩል እድለኛ ነኝ፤ ፈጣሪ እረድቶኛል፡፡ ለምሳሌ “አርት ቴራፒ” በሚል ለጋምቢ ሆስፒታል ፕሮፖዛል አስገብቼ መልስ እየጠበቅኩ ነው፡፡
“አርት ቴራፒ” ምንድን ነው?
አንድ ታማሚ በተኛበት የሆስፒታል ክፍል ፊት ለፊቱ አንድ ማራኪ ስዕል ቢሰቀል፣ ያንን ስዕል በማየትና በመመራመር፣ ህመሙን ለአፍታ ያህል ቢረሳ ቀላል አይደለም፤ የጎንዮሽ ጉዳት የሌለው መድሀኒት ነው፤ ስለዚህ በዚህ መልኩ ስዕሎችን ሰርቼ ህመምተኞች ክፍል ለመስቀል ምክረ ሀሳብ ባህርዳር ለሚገኘው ጋምቢ ሆስፒታል አቅርቤያለሁ። ምን ለማለት ነው… ያሉትን አማራጮች ሁሉ እሞክራለሁ፤ ከማንኳኳቸው 10 በሮች አንዱ ይከፈታል፡፡
በአሁኑ ወቅት በጉራማይሌ አርት ጋለሪ “ነቁጥ” የተሰኘ የስዕል አውደ ርዕይ ለዕይታ አቅርበሃል፡፡ ስራዎችህ ሁሉ የተሰሩት ደግሞ በከብት ቆዳ ላይ ነው። የስዕል (art) ፍልስፍናህ ምንድን ነው?
እንግዲህ የእኔ አርት ፍልስፍና የምለው ገና በሂደት ላይ እንዳለ ይሰማኛል፡፡ እኔ እንደ ትልቅ ነገር የማነሳው፣ በዚህኛው በ“ነቁጥ” ብቻም ሳይሆን ከመጀመሪያው አንስቶ በነበሩ ሥራዎቼ ጎልቶ የሚታይ ነገር አለ፡፡ “ተቃርኖን ማስታረቅ” የሚል ነው፡፡ ሁለት በሀሳብ፣ በቅርፅና በቀለም የሚለያዩ ነገሮች አንድ ላይ የሚሆኑበት ክፍል ፈልጎ፣ የማቀራረብና ማስታረቅ አካሄድ ነው። ለምሳሌ ኢትዮጵያ የምትባለው አገር በአስደማሚ ተቃርኖዎች የተሞላች፤ ነገር ግን ተቃርኖዎቿ ጌጥ የሆኑላት አገር ናት፡፡ ለአብነትም ዳሎል በጣም የአገሪቱ ዝቅተኛ ቦታ ነው፣ ራስ ዳሽን ከአፍሪካ በከፍታው ሁለተኛ ደረጃ  ላይ የሚገኝ ትልቅ ተራራ ነው፡፡ ሁለቱ በአንድ አገር በጣም በተቃርኖ ደግሞም ውበት ሆነው ተቀምጠዋል፡፡
ለእኔ ምዕራባዊ የሆነው አጠቃላይ ፍልስፍና “ትራዲሽናል” ሲል ያስቀኛል፡፡ ዘመናዊነት (ሞደርኒቲ) የባህላዊ ሂደቶች ቅጥያ ነው እንጂ በተለየ ሁኔታ የተፈጠረ አይደለም፡፡ ቀደም ብሎ የነበረው ባህላዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ሂደት ቀስ በቀስ እየተቀየረ ይሄዳል እንጂ በአንዴ ብጥስ ብሎና ከባህላዊነቱ ተለይቶ ብቻውን የቆመ አይደለም፡፡ ስለዚህ ዘመናዊነት ራሱን ለማስቀጠል አሁንም ባህላዊነት የግድ ያስፈልጋል፡፡ እኔ በስራዬ በአብዛኛው ባህላዊ ኤለመንቶችን እወስዳለሁ። በዚያው ልክ በጣም ዘመናዊዎቹንም እወስድና በጣም አስታርቄ አንድ የተጣጣመና የተቀናጀ ነገር እፈጥራለሁ። ብዙ ስራዎቼ ላይ የሚታይ ባህርይ ነው፡፡ ፈጣሪ በስራዎቹ ላይ የገለፀውም ይህንን ውበት ይመስለኛል፡፡ ይሄ ነገር ነው እንዳይሰለቸን የሚያደርገው፡፡ አሁን ቅጠል አንድ አይነት ተመሳስሎ ይኖረውና በዚያ ውስጥ ልዩነት አለው። ፋብሪኬትድ የሆነ ወይም ሰው የሰራው ነገር ነው ቶሎ የሚሰለቸው፡፡ ይሄ ከፈጣሪ የወሰድኩት ትልቅ ጥበብ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ሰው ሁሉ በፈጣሪ ሊነቃቃ ይችላል፡፡ በተፈጥሮ ብቻ ወይም በተለያየ ነገር ሊነቃቃም ይችላል፡፡ እኔ በራሱ በፈጣሪ ነው የተነቃቃሁት፡፡ እንደ አምላክ ከማምለክ በዘለለ  እንደሚጠበብ ሰው “creative-personality” አድናቂው ነኝ፡፡
“ነቁጥ” በሚል በሰየምከው  አውደ ርዕይህ ላይ ስራዎችህ ለምንድን ነው በከብት ቆዳ የተሰሩት? “ነቁጥ” ስትል የሰየምከውስ በምን ምክንያት ነው?
እኔ ወደ ቆዳ አርት የገባሁት መጀመሪያ እንደ አንድ ገጠር እንደተወለደ ልጅ፣ ከበሬና ላም ጋር ያለኝ ግንኙነትና ቅርበት የጠበቀ ነው፡፡ እንደውም አያቴ ስታሳድገኝ “ትርባልኝ” የምትባል ላም ነበረች፤ለእኔ ብቻ የተመደበች፡፡ ቀጥታ አፌን ከፍቼ፣ አያቴ ወተት አፌ ላይ እደረገች ነው ያሳደገችኝ፡፡ ከዚህ አለፍ ብዬ በሬን መመልከት ጀመርኩ፡፡ በሬ እየተገረፈ አርሶ ያበላል፣ ከዚያ ስጋውን ይሰጣል፡፡ ቆዳውን ለገመና መሸፈኛ ይሰጣል፡፡
በመፅሐፍ ቅዱስ አማኒያን ዘንድ ለመጀመሪያ ጊዜ ሰው በሀጢያቱ ምክንያት ፀጋውን ተገፍፎ፣ ራቁቱን ሲቀር ገመናው ለመሸፈን የተጠቀመው ቅጠል ነው። ነገር ግን ቅጠል ረጅም ጊዜ ስለማይቆይ ጌታ ራሱ ቆዳ ነው የሰጣቸው፤“ለምድ አለበሳቸው” ይላል፡፡ ቀንዱን ለመጠጫ፣ ጅራቱን ለመግረፊያ እንጠቀማለን፡፡ በፖለቲካዊ አንድምታም ከሄድን፣ ነጋሪት ተጎስሞ አዋጅ የሚነገረው ከበሬ ቆዳ ተሰርቶ ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ እበቱ ራሱ ማገዶ ይሆናል፡፡
በሬ ቁርጥምጥም አድርገን የምንጠቀመው ፍጥረት ነው፡፡ ለዚህ ሁሉ ፈቃደኛ የሆነም ነው፡፡ ይህ ነው መነሻዬ፤ ቆዳ ላይ ያተኮርኩበት፡፡ በሬ ያ ሁሉ ቆዳው ላይ ያለ ዥንጉርጉር፣ ትልቅም ይሁን ትንሽ ነቁጥ፣ ብዙ በሬ አያደርገውም፤ እነዛ ተባብረው ነው በሬ የሚያሰኙት፡፡ ይህ እሳቤ የበለጠ ስለሳበኝ ነው ያተኮርኩበት፡፡
በተለይ በገጠር አካባቢ ቆዳ ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ነው ያለው---
እውነት ነው፡፡ የገጠሩ የቆዳ አጠቃቀም ከተነሳ አይቀር በጣም የሳበኝ፣ አጎዛውን ግድግዳ ላይ ሰቅለው፣ ለጌጥና ለአይን ማረፊያ ያደርጉታል፡፡ ከዚያ ያወርዱና አንጥፈው ይተኙበታል፡፡ ሲተኙ ደግሞ ያሸትቱታል፡፡ እነዚህ የውበት ልምምዶች ሁለት አይነት ነገር አላቸው፤ ተግባራዊም ውበታዊም። እነዚህን ሁለት መልክ ያላቸው ስራዎች ለእይታ ማቅረብ በምዕራባዊያን አረዳድ፤ “ማቴሪያል ካልቸር” ነው የሚሉት፡፡ ምን ማለት ነው? ሰው ለዕለት ተዕለት ኑሮው የሚጠቀምባቸው እንጂ የተጠበበት አርት አይመስላቸውም፡፡ እንደኔ እምነት ግን ሙዚየም ባለማቅረባቸው እንጂ እነዚህ ስራዎች በምዕራባዊያን ሙዚየሞች ከሚታዩ ስዕሎች በላይ ጠንካራ ናቸው፡፡
እንደውም አሁን በዘመናዊ ስነ-ጥበብ ትልቁና ጠንካራ መሆን አለበት የሚባለው አርቲስቱ በአይን ታይቶ ከሚያበቃና ዋው ከሚያስብል ስራ በዘለለ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የሆኑ ጉዳዮችን የሚያነሳ፣ የሚቀሰቅስና የሚታገል ነው። እነዚህ አርቲስቶች ከእለት ተእለት ህይወታቸው ጋር የተቆራኙ ነገሮችን ወስደው ለታይታና ለእይታ ብለው ሳይሆን ከልብ የመነጨ ሀሳባቸውን ያንጸባርቁባቸዋል፡፡ ለነዚህ ስራዎች ደግሞ ቦታ ተሰጥቶ መካተት አለባቸው የሚል ሀሳብ ይዤ  ነው የተነሳሁት፡፡
ታዲያ ስራዎችህ ተቀባይነት አግኝተውልሃል?
አሁን ይሄን የሚደግፉልኝ ሱዛን ፎግል፣ ካሮል ዳንከል እና ሌሎችም ፀሀፊዎች አሉ፡፡ እነዚህ ፀሀፊዎች የአፍሪካዊያን አርት በምዕራባዊያን ሙዚየም ለእይታ ሲቀርብ እንደ እቃ ነው የሚከለኮለው እንጂ እንደ ሪፋይን አርት በስርዓቱና በክብር አያቀርቡትም፡፡ የራሳቸውን ግን ከአምላክና ከሰማይ የወረደ አድርገሽ እንድትመለከቺው፣ ያንን ስሜት ይፈጥሩብሻል፡፡ እኔ እንደምታዪው፤ እነዚህን ሞሰቦች፣ አገልግሎችና ሌሎች እቃዎችን ከእቃነት በዘለለ ራሳቸው ጥልቅ የሆነ ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ እሳቤ ያላቸው መሆኑን ለማሳየት ሞክሬያለሁ፡፡ ቅድም የጠቀስኩልሽ ፀሀፊዎች፣ይህንን ስራና አስተሳሰብ ይደግፉታል፤ተቀባይነቱ የሚያጠራጥር አይደለም፡፡
በአውደ ርዕዩ ላይ ከቀረቡት መካከል የገረመኝ፣ ትልቁ በቆዳ የተለበጠው መሶብ፣ በቁልፍ ተቆልፎ በርካታ የቁልፍ መክፈቻዎች ከበውታል፡፡ እስቲ የዚህን መሶብና የቁልፍ መክፈቻዎቹን ምስጢር አብራራልኝ?
በዚህ መሶብና በቁልፉ ማስተላለፍ የፈለግኩት እንጀራ፣ ተስፋና ዕድልን ነው፡፡ የእቃዎቹን አቀራረብ installation (ኩልኩል) እንለዋለን። ጥልቅ የሆነውን የሰው ህይወትና በሕይወቱ የሚገጥሙትን ጉዳዮች ሊገልፅ በሚችል መንገድ የምናስቀምጥበት ነው:: ሰው ተስፋ አለው፣ ዕድልም አለው፣ እንጀራም አለው፡፡ ተስፋው ያለ ማቋረጥ ይሄንን ቁልፍ ለመክፈት እንዲሞክር ያደርገዋል። ዕድሉ ሙከራውን ያሳካለታል፡፡ እንጀራው በነዚህ ሂደቶች የሚገኝ ስኬት ነው፡፡ ይህ የተቆለፈ መሶብ በስሩ ከተደረደሩት መዓት ቁልፎች አንዱ ይከፍተዋል። የሚከፍተው ቁልፍ ምንም ምልክት የለውም፡፡ ይሄ የብዙ ሰዎችን ሀሳብ ይሞግታል፡፡
በምን መልኩ?
ቁልፉ ከእነዚህ ቁልፎች መሀል እንዳለ እናውቃለን። የሰው ልጅ ከእነ ዕድሉ፣ ከእነ ስጦታው ነው የተፈጠረው፤ ነገር ግን አብዛኛው የሚሞክርና የሚጥር አይደለም፡፡ አንድ ሰው ተስፋ ካደረገ፣ ከጣረ ዕድሉ ቁልፉን እንዲያገኝ ያደርገዋል። ይሄ ሙግት በውስጥሽ መመላለሱ አይቀርም፡፡
ለጉብኝት የሚመጡ ሰዎችን የዚህን ሞሰብ ቁልፍ ሞክረው እንዲያገኙ ስትጋብዝ አይቻለሁ። እኔም በርካታ ቁልፎችን ሞክሬ መሶቡን መክፈት አልቻልኩም፡፡ ለመሆኑ እስካሁን ሞክሮ የተሳካለትና የከፈተው አለ?
የሚገርምሽ አንድ ልጅ ሞክሮ ተሳክቶለታል፡፡ በውስጡ ምን አገኘ የሚለውን አሁን አልናገረም፤ ነገር ግን ይሄ ልጅ መክፈት አለብኝ ብሎ ቆርጦና ወስኖ ነው የተቀመጠው፡፡ ልጁ ምን ያህል ሰዓት  ታግሶ ወስኖ እንደተቀመጠ ስመለከት፣ የልጁ ቁርጠኝነት ለብዙ ሰው ትምህርት የሚሆን ነው። ህፃናትም በብዙ ትዕግስት ፈልገው ፈልገው፣ “እባካችሁ የትኛው ነው፣ አሳዩን?” እስከ ማለት ደርሰዋል፡፡
አንተ ግን ቁልፉ የትኛው እንደሆነ ታውቀዋለህ?
በፍፁም! እኔም አላውቀውም፡፡ አንድም የሌላው ህብረተሰብ አካል ለመሆን፣ በሌላም በኩል ለራሴ እንዳላዳላ በሚል አላውቀውም፡፡ እንግዲህ በምዕራቡ ዓለም ስዕል በእጅ አይነካም፤ አይዳሰስም፤ በቃ ሀይማኖታዊ ነገር አድርገው ነው የሚያስቀምጡት። አምስት ሜትር ከስዕሉ ርቀሽ ነው የምትመለከቺው። እኛ ጋ ትነኪዋለሽ፣ ትዳስሺዋለሽ፣ የሰቀልሺውን ራሱ አውርደሽ ትተኚበታለሽ፤ ስለዚህ የሚዳሰስ የሚታይና የሚሸተት ሥራ ነው የምንሰራው፡፡
አውደ ርዕዩን ብዙ የውጭ ዜጎች ሲጎበኙት ተመልክቻለሁ፡፡ ጎብኝዎች የሰጡህ አስተያየት ምን ይመስላል?
ያገኘኋቸው ሁሉ በጣም ፍላጎት ያሳደረባቸው ነገር ምን መሰለሽ? ወይ ዘመናዊነቱ ውስጥ ጥልቅ ብለህ አልገባህ ወይ በጣም ባህላዊ በሚባል መንገድ አልመጣህ፤ ሁለቱን አቻችለህ ስለምትሞግተን እኛም የሀሳብ ለውጥ ለማድረግ ተመችቶናል፡፡ በሌላ በኩል በአይን ከመታየት አልፎ እንድንነካ፣ አገላብጠን እንድናይ ዕድል አግኝተናል፡፡ የሚዳሰስ የሚሸተት የሚታይ ስዕል ማየታችን አዲስ ስሜት ፈጥሮብናል ሲሉ  ተናግረዋል፡፡
ሌላ መናገር የምፈልገው ነገር፣ በምዕራባዊያን ፕላት ፎርም ውስጥ የተካተተው የስነ- ጥበብ ፍልስፍና እና ታሪክ የሌላውን አለም ያላቀፈ ነው የሚል ሙግት አለ። እነ ፒካሶ በተነሱበት ዘመን በተጓዳኝ በአፍሪካ፣ በላቲን አሜሪካ፣ ከምዕራቡ ተመጣጣኝ የሆኑ የአርት ክንውኖች የነበሩ ቢሆንም የተካተተው የምዕራቡ ብቻ ነው የሚል የሀሳብ ፍጭት ስላለ፣ በዚያ ሙግት ውስጥ የእኔን ትንሽ ነፀብራቅ ለማሳየት ነው እየሞከርኩ ያለሁት፡፡
በስዕሎቹ በቆዳ የተለበጠ ቴሌቪዥን ተመልክቻለሁ። ትርጉሙ ምንድን ነው?
ቴሌቪዥን በአገራችን የማህበረሰብን ስትራክቸር የቀየረ ነው፡፡ ምን ማለት ነው--- ቀደም ባለው ጊዜ ቤት ውስጥ ስንቀመጥ፣ ትልልቅ ሰዎችን ከብበን ነበር፡፡ ማዕከል የሚሆኑት እናት አባቶቻችን ናቸው። አሁን ደግሞ ቴሌቪዥን ከበን ነው የምንቀመጠው፡፡ የቴሌቪዥኑ አቀማመጥ ደግሞ ለሁሉም ለህፃን ለአዋቂው እንዲመች ተደርጎ ነው የሚዘጋጀው፡፡ ዱሮ ተረት፣ ምክር የምንሰማው ከታላላቆቻችን የሚጠቅመንን ብቻ ነበር፡፡ አሁን ቴሌቪዥን የምናየው ያለ ዕድሜ ገደብ ነው፡፡ ለልጅ ነው ለአዋቂ ነው የለም፣ ያውም ተገምግሞ በማያልፍ የትኛውም ሀሳብ ውስጥ አብረን እንሰለፋለን፡፡ ይሄ ለእኔ አስጊ ነው፡፡ ቴሌቪዥኑን ቆዳ ያለበስኩት፣ ከቴሊቪዥኑ የሚወጣውን እኛ ብናስተካክለውና ብንዋጀው የሚል ምኞቴን ለማስተላለፍና የሚጠቅመንን ብቻ የምንሰማበት ልናደርገው ብንችል የሚለውን ህልሜን ለማሳየት ነው፡፡ እንግዲህ የሀሳብ ተቃርኖውን የሚያሳይ ነው። ቆዳው የእኛ ነው፤ ቴክኖሎጂው የእነሱ ነው። ይሄ በእጄ የያዝኩት ስልክ ጥሩም መጥፎም አይደለም፤ በስልኩ የምጠቀምበት ነገር ነው ጥሩና መጥፎ ሊያሰኘው የሚችለው፡፡ በስልኩ ደውዬ “ሰው ግደል ወይም የወደቀ ሰው አንሳ” ስል ውጤቱ ይወሰናል ማለት ነው፡፡
አሁን ደግሞ በአሜሪካ ስላሳየኸው አውደ ርዕይ  እና በቅርቡ በግብፅና በኢኳዶር ስለምታሳየው የስዕል አውደ ርዕይ አጫውተኝ ----
ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ፣ አንድም ቀን ታዋቂ ለመሆን ብዬ ከአርት ጋር ተቆራኝቼ አላውቅም፤ ነገር  ግን በፍቅርና በፍላጎት ተሞልተሽ ስትሰሪ፣ አይን ውስጥ ትገቢያለሽ፡፡ በመጀመሪያ ያገኘሁት እድል በአሜሪካ ላስቬጋስ በኔቫዳ ዩኒቨርሲቲ የሚገኝ የስነ-ጥበብ ተቋም ነው፡፡ በማይመች አካባቢ ውስጥ ሆኜ በባህርዳር ለአምስት ዓመታት ሥነ-ጥበብ ላይ በመስራቴ በተለይም ከወጣሁበት አካባቢ ሀይለኛ ግንነት ያለው ስራ መፍጠር በሚል “ፐብሊክ ሌክቸር” ሳደርግ፣ በተጨማሪም ስራዎቼን “ባሪክ” ሙዚየም ውስጥ ከንግግሬ ጎን ለጎን ለእይታ አቅርቤ ነበር፡፡ ከዚያም ለሶስት ሳምንታት ያህል ግራንት ሆል ጋለሪ ሆል ውስጥ ስራዎቼ ለእይታ በቁ፡፡ ቦልደርሲቲ በሚባል ከተማም ስራዎቼ ለህዝብ ለእይታ በቁ፡፡ በዚያው ከተማም ለህዝብ ንግግር አድርጌአለሁ። ይሄ በጣም ያስደሰተኝ ኢትዮጵያን የማያውቁ ሰዎች ገጥመውኝ ነበር፡፡ በእኔ ስራ ምክንያት ኢትዮጵያን ማወቃቸው ትልቅ ደስታ ፈጥሮብኛል፡፡ እነ ኃይሌ ገ/ሥላሴን እያወቁ ኢትዮጵያን አያውቁም፡፡ ለእነዚህ ሰዎች ስለ ኢትዮጵያ መናገሬ ያስደስተኛል። እርግጥ ነው ስሄድ አበባ ይዞ የተቀበለኝ የለም፤ የሰራኋቸውን ለእይታ ያቀረብኳቸውን ስራዎቼን ብዙ ግምት ውስጥ ያስገባ የለም፤ ሆኖም ኢትዮጵያን አስተዋውቄያለሁ፡፡ እርግጥ ሲጠሩኝ ከወጣሁበት አካባቢና ባህል ጋር የተቆራኘ ሥራ በመስራቴ ሁኔታዎች በማያበረታቱበት ድባብ፣ በፈተና ውስጥ ያለማቋረጥ የስዕል አውደ ርዕይ ለአምስት ዓመት በማቅረቤ ነው፡፡ በባህርዳር በቆየሁባቸው በነዚህ ጊዜያት አመታዊ አውደ ርዕዮች እንዲኖሩ አድርጌያለሁ፡፡
ሁለቱ ላይ በተለይ የአዲስ አበባ አርቲስቶች እንዲሳተፉ በማድረግ፣ ባህርዳርን አማራጭ የስነ-ጥበብ ማዕከል የማድረግ ህልሜን ለማሳካት ሙከራዬን የጀመርኩበት ነው፡፡ “ጥበበ ባህርዳር” “አርት ኦፍ ዘ ናይል” በተሰኙ ኤግዚቢሽኖች ነው ይህን የሰራሁት። በኋላም በግሌ ሦስት ኤግዚቢሽኖች አቅርቤያለሁ፡፡ በብሔራዊ ሙዚየምም “ሀገረ ቀለም ኢትዮጵያ” የተሰኘ በሀሳብም፣ በቴክኒክም ሆነ በቀለም በዛና ተለቅ ያለ ኤግዚቢሽን ነበረኝ። አሁን በሶሻል ሚዲያም በርትቼ እየሰራሁ ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎችም በኔ ተነቃቅተው እየፃፉ ይገኛሉ። ናይጄሪያ በሚታተም “ታይምስ” የተሰኘ መፅሄት ላይ “ዘ አርቲስት ኦፍ ናሽናል ኮንሺየስነስ” በሚል ርዕስ ሽፋን አግኝቻለሁ፡፡
በግብፅና በኢኳዶር ስለምታቀርበው አውደ ርዕይ ንገረኝ---?
በኢኳዶር የሚካሄደው ዓለም አቀፍ ሰሚት ነው። በግብፅ ደግሞ “ኢንተርናሽናል አርት ሲምፖዚየም” ከአፕሪል 12 እስከ 24 ቀን 2018 ይካሄዳል፡፡ በዚያ ላይ እሳተፋለሁ፡፡ በዚህ ሁሉ ደስኛ ነኝ፡፡ አገራችን የ3 ሺህ ዓመት ታሪክ ያላትና የባህልና ታሪክ አገር መሆኗ፣ ለአንድ የፈጠራ ሰው በተለይ በስነ-ጥበብ ሙያ ውስጥ ላለ ሰው እድለኝነት ነው፡፡ ብዙ የምንሰራበት እድል አለ፡፡ ህልሜ ስዕልን ለእይታ አቅርቦ ከመሸጥ በዘለለ ጠንካራ ንቅናቄ ለመፍጠር ነው፡፡ ይህ ደግሞ ይሳካል፡፡  


 “--አጎዛውን ግድግዳ ላይ ሰቅለው፣ ለጌጥና ለዓይን ማረፊያ ያደርጉታል፡፡ ከዚያ ያወርዱና አንጥፈው ይተኙበታል፡፡ ሲተኙ ደግሞ ያሸትቱታል፡፡ እነዚህ የውበት ልምምዶች ሁለት አይነት ነገር አላቸው፤ ተግባራዊም ውበታዊም፡፡--”

    ተወልዶ ያደገው በጎጃም ገጠር ቢሆንም ያደገውና የተማረው በባህርዳር ከተማ ነው - ሰዓሊ እያዩ ገነት፡፡ የመጀመሪያ ድግሪውን ከባህርዳር ዩኒቨርሲቲ በኢኮኖሚክስ ቢያገኝም የነፍሴ ጥሪ እንዳልሆነ ስገነዘብ፣የወርልድ ቪዥን ሥራዬን ጥዬ፣ ወደ አዲስ አበባ መጣሁና የስዕል ት/ቤት ገባሁ ይላል፡፡ በትምህርቴ “ሰቅዬ” በመቅረት በስዕል    ት/ቤት ውስጥ የተወሰነ አበርክቶ ይኖረኛል የሚል እምነት ነበረኝ የሚለው ሰዓሊው፤ ነገር ግን በተለያዩ ምክንያቶች ሳይሳካ ቀረና የሀይስኩል ተማሪዎችን በራሴ ተነሳሽነት፣ ስዕል ማስተማር ጀመርኩኝ ብሏል፡፡ በፋይን አርት ዲግሪውን ከአገኘ በኋላስ? የጥበብ ጉዞው ምን ይመስላል? ወደ ባህርዳር ይዤው ሄድኩ ስለሚለው ህልሙ ያወጋናል፡፡ ስዕል እንጀራ አይሆንም በሚል የሚንጸባረቀውን  አመለካከትም ይሞግታል። ስለ ምዕራቡ ዓለም የሥነ ጥበብ ፍልስፍና፣ “ነቁጥ” በሚል ስያሜ በጉራማይሌ የሥነጥበብ ጋለሪ ለዕይታ ስላቀረበው አውደ ርዕይ ያብራራል፡፡ ሰዓሊው በቅርቡ በግብጽና በኢኳዶር በሚካሄድ የሥነ ጥበብ ሲምፖዚየም ላይ እንደሚሳተፍም ይገልጻል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ሰዓሊውን በጥበብ ህይወቱ ዙሪያ አነጋግራዋለች፡፡ እነሆ፡-  


   ስሜትህ ለስነ-ጥበብ እያደላ እንዴት ኢኮኖሚክስ ለመማር ዩኒቨርሲቲ ገባህ?
“ብልጥ ልጅ እየበላ ያለቅሳል” ይላሉ አበው። በውስጤ የስነ-ጥበብ ፍቅር ቢኖረኝም አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተገብቶ መማር እንደሚቻል የነገረኝ ወይም መንገዱን ያሳየኝ አልነበረም፡፡ ብቻ ባህርዳር ላይ ዘውዱ ባይሌ የሚባል ሰዓሊ ነበር (ነፍሱን ይማርና) ጋለሪ ከፍቶ የማስታወቂያ ስራ ሲሰራ እያየሁ፣ እሱን ነበር መሆን የምፈልገው፡፡ ነገር ግን በወቅቱ የትምህርት ውጤቴ ጥሩ ስለነበር ካሉት ትምህርቶች የተሻለ ነው ብዬ ያመንኩትን የኢኮኖሚክስ ትምህርት ልማር ቻልኩኝ፡፡
በተማርከው ትምህርት ሰራህበት ታዲያ? ከዚያስ እንዴት ወደ አለ የስነ ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት ገባህ?
በኋላ ላይ ጥሪሽ እንዳልሆነ ሲገባሽ ሁሉም ነገር ትግልና ፈተና ይሆንብሻል፡፡ ላልተፈጠርንበት አላማ ምናልባት ችለን በእጃችን ልንሄድ እንችላለን ግን እጅ እንደ እግር እንደማይሆን የተረዳን ሰዓት፣ በእግር መሄድ ስንሞክርና በጣም ምቹ መሆኑን ስንረዳ በእጃችን የሄድንበትን ጊዜ እንፀፀትበታለን። ምን ለማለት ነው… ለአፍንጫም ለአይንም አሁን ካለበት የተሻለ ቦታ የለም። በኢኮኖሚክሱ ሰርተህበታል ወይ ላልሺኝ፤ እርግጥ ነው ወርልድ ቪዥን ገብቼ ስራ ጀምሬ ነበር፡፡ ነገር ግን ለዚያ ቦታና ስራ የተፈጠርኩ አለመሆኔ ሲገባኝና የነፍሴ ጥሪ አርት እንደሆነ ስረዳ፣ ወደ አዲስ አበባ መጥቼ አርት ት/ቤት ገባሁ፡፡ በወቅቱ ቤተሰቤም እንጀራ ትተህ ሄደህ እንጀራ አይወጣልህም ብለውኝ ነበር፤ ደስተኞችም አልነበሩም፡፡ እኔ ግን ትዝ ይለኛል፣ ወደ አዲስ አበባ ስመጣ በኪሴ የነበረው 300 ብር ብቻ ነበር። ጫማ ጠርጌም ቢሆን የተጠራሁበትን ዓላማ አሳካለሁ የሚለውን ህልም ይዤ ነው የወጣሁት። ከዚያ አራት አመት በአርት ስኩል ትምህርቴን ስከታተል ቆይቼ፣ በፋይን አርት ዲግሪዬን አገኘሁ፡፡
በስዕል ት/ቤት በነበረህ ቆይታህ ከመደበኛው ትምህርት ውጭ በራስህ ላይ የጨመርከውን ነገር ንገረኝ…?
እንደኔ አመለካከት ትምህርት አንቺን አይፈጥርሽም ግን የተፈጠረውን አቅምሽን ቅርፅ በመስጠትና አቅጣጫ በማስያዝ ከፍተኛ እገዛ ያደርግልሻል፡፡ እኔ በተለይ ከመምህራኖቼ በጣም የሚያስገርሙ አቅሞችን አግኝቻለሁ፡፡ እነ መዝገቡ ተሰማ፣ ታደሰ መስፍን፣ ጌታሁን አሰፋ፣ በቀለ መኮንንና ሌሎችም አመለካከትን ሊቀይሩ ከሚችሉ ሰዎች ጋር የመገናኘት ዕድል ማግኘትሽ ያለሽን ነገር ጥልቀት ይጨምርልሻል፡፡ በዚህ ምክንያት ለሙያው ያለኝ ጥማት ጨርሶ ነደደ፡፡ መጀመሪያም ፓሺን ነበረኝ፤ ትምህርቱ ደግሞ የበለጠ ፍቅርና ፍላጎቱን አቀጣጠለልኝ፡፡ እርግጥ ነው መጀመሪያ ላይ የሚያሳጣሽ ነፃነት አለ…፡፡
ምን አይነት ነፃነት ነው የሚያሳጣው?
የምንማርበት ሥርዓተ ትምህርት የተቀረፀው በምዕራቡ አስተሳሰብ ላይ ማዕከል አድርጎ በመሆኑና የአገራችንን ነባራዊ ሁኔታ ከግንዛቤ ውስጥ ስለማያስገባ በጣም ገዳቢ ነው፡፡ ነገር ግን አንቺ ብልህ ከሆንሽ ያንን ትምህርት ከራስሽ ሁኔታ አንፃር እየቃኘሽ መጠቀም ትችያለሽ፡፡ እኔም በት/ቤት ቆይታዬ ይህንን ሳደርግ ነው የቆሁት፡፡ ከዚያ በኋላ በነበረኝ ፍቅር… በውጤቴ ምክንያት እዚያው ት/ቤት በመምህርነት እቆያለሁ የሚል እምነት ነበረኝ፡፡ እንደው እዚያው ጨርሶ መቅረትም ባይሆን እንኳን የተወሰነ አበርክቶ ይኖረኛል የሚል ሀሳብ ነበረኝ፡፡ ነገር ግን በተለያዩ ምክንያቶች ሳይሳካ ቀረና የሀይስኩል ተማሪዎችን በራሴ ተነሳሽነት፣ ደስ ብሎኝ ስዕል ማስተማር ጀመርኩኝ። ይህን እያደረግኩኝ ዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ አርኪቴክቸር ዲፓርትመንት የማስተማር ዕድል አገኘሁ፡፡ እዛም ለአንድ ዓመት ያህል ሰራሁ፡፡
ብዙ የስዕል አውደ ርዕዮች ላይም ተሳትፈሃል…?
አውደ ርዕዮችን--- በአሊያንስ ኢትዮ ፍራንሴዝ፣ በጎተ ኢንስቲትዩት፣ በአሜሪካ ኤምባሲና በሌሎች ቦታዎች በቡድን አቅርቤአለሁ፡፡ ይህንን ሳደርግ ግን የቀደሙ አርቲስቶች የሚሰሩትን እንደምደግም እንጂ አዲስ ነገር እንደማልሰራ ተረዳሁ፡፡ ከዚያ አንድ ህልም ይዤ ወደ ባህርዳር ሄድኩኝ፡፡ እንደምታውቂው አለ የስነ-ጥበብና የዲዛይን ት/ቤት 50 ዓመት ሞልቶታል፡፡ ከዚያ የሚወጡ አብዛኞቹ ሰዓሊዎች እዚህ አዲስ አበባ ነው የሚሆኑት። ምክንያቱም አዲስ አበባ የብዙ ኤምባሲዎች፣ የዲፕሎማቶች መቀመጫ በመሆኗ ገበያው ያለው እዚሁ ስለሆነ ነው፡፡ ወደ ክልል አይወጡም፡፡ ክልል ላይ ደግሞ በተደራጀ መልኩ የሚካሄድ የአርት እንቅስቃሴ የለም፡፡ እኔ ደግሞ ባህርዳር ያደግኩባት ከተማ ናት፡፡ ቤተሰቦቼም ያሉት እዚያው ናቸው፡፡ ስለዚህ ባህርዳር የቱሪስት ከተማ በመሆኗ አማራጭ የስነ ጥበብ ከተማ (Alternative Art corner) የማድረግ ህልም ይዤ ወደ ከተማዋ ተመለስኩኝ። እድለኛ ነኝ፤ ባለቤቴም ስራዋን ትታና ህልሜን ተከትላ አብራኝ መጣች፡፡ ከዚያም አንድ ት/ቤት ውስጥ ማስተማር ጀመርኩኝ፡፡
በባህርዳር ዩኒቨርሲቲ የአርኪቴክቸር ዲፓርትመንት የአርት ኮርሶችን ትሰጣለህ አይደል?
ትክክል ነው፤ አስተምራለሁ፡፡ ቅድም ያልኩሽ ት/ቤት እያስተማርኩ እያለሁ አቫንቲ ብሉናይል ሆቴል፣ አሁን ብሉናይል ሪዞርት ሆቴል ሆኖ የተቀየረው አንድ ነገር አደረገልኝ፡፡ አንድ ቀን፤ “ፈጣሪ እባክህ ያለምኩትን አሳካልኝ” ብዬ ፀሎት አደረግሁኝ፡፡ እኔ ህልሜ ታዋቂ ለመሆን አይደለም፤ ብዙ ብር ለመሰብሰብ አይደለም፤ ግን ይህ ህልሜ የእውነት መስመር እንዲይዝ እፈልጋለሁ” አልኩና ፀልዬ ወደ ነገርኩሽ ሆቴል ሄድኩኝ፡፡ ሀላፊው ሚስተር ስቴቨን ይባላል፤ አገኘሁት፡፡ በሚገርም ሁኔታ ሆቴሉ መቶ ሺህ ብር ስፖንሰር አድርጎኝ፣ 50 ያህል ስራዎችን ማቅረብ ቻልኩኝ፡፡ ካቀረብኳቸው ስራዎች ውስጥ እድለኛ ሆኜ፣ ከ20-30 ያህሉ ስዕሎች ከ2-7 ሺ ብር በሚደርስ ዋጋ ተሸጡ፡፡ በዚህ ውጤት ህይወቴን፣ ከቤተሰቤም ጋር ያለውን ነገር አስተካከልኩኝ፡፡ በርካታ ጉዳዮችን ከወንኩኝ፡፡
በዚህ መሃል የቀድሞው የባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ባይሌ ዳምጤ፣ በስዕል ኤግዚቢሽኑ ስነ-ስርዓት ላይ ከባለቤታቸው ጋር ታድመው ነበርና፣ “ከተማችን እንዲህ አይነት ልጅ አለን እንዴ? ለአርኪቴክቸር ዲፓርትመንት ብዙ ጊዜ ማስታወቂያ አውጥተን አላገኘንም” ብለው ሪኮመንድ አደረጉኝ፡፡ ቅድም እንዳልሺው በዩኒቨርሲቲው ማስተማር ጀመርኩኝ ማለት ነው። ለሙያው ካለኝ ፍቅር የተነሳ ተማሪም እያለሁ፣ ሁለት ክረምቶች 80 ያህል ወጣቶችን በስዕል ትምህርት በበጎ ፈቃደኝነት አሰልጥኛለሁ፡፡  ከነዚህ መካከል ከ10 በላይ ሰልጣኞች፣ አለ የስነ ጥበብ ዲዛይን ትምህርት ቤት ለመግባት ችለዋል፡፡ ይሄም እድለኛ ነኝ ያሰኘኛል፡፡ አሁን ልጆቹ በጥሩ ሁኔታ እየተንቀሳቀሱ ነው፡፡ በዚህ በጣም ደስተኛ ነኝ፡፡
እኛ አገር ላይ ስዕል እንጀራ አይሆንም የሚለው አመለካከት በስፋት ይንፀባረቃል፡፡ አንተስ ይህን አመለካከት  ትጋራዋለህ?
ምን መሰለሽ… እንጀራ ይሆናል ብለሽ፣ እንጀራ እንጀራውን እያሰብሽ ከገባሽበት እንጀራ አይሆንም። ነገር ግን ሙያውን የእውነት ወደሺው፣ ራስሽን ሰጥተሸ ከልብሽ ስትሰሪ እንጀራ መሆን ይጀምራል። ስለዚህ ሙያችንን ወድደነው፣ በፍቅርና በትጋት ነወይ የምንሰራው? የሚለው ጥያቄ መመለስ አለበት፡፡ ሙያችንን ወድደን ራሳችንን ሆነን ሥንሰራ፣ የማንንም አንገለብጥም፡፡ ስለዚህ ትኩረት እንስባለን፡፡ አሁን ሰው ለአርቱ ያለው አመለካከት እየተቀየረና አይኑ እየተከፈተ ነው። እኔ ለምሳሌ ሙያዬ በአንድ አቅጣጫ ብቻ ገቢ እንዲያመጣልኝ አልፈልግም፡፡ የህትመት ስራዎች ሰርቻለሁ፣ ዲዛይኖች ሰርቻለሁ፡፡ ጨጨሆ የባህል ምግብ አዳራሽን ካየሺው፣ የባህርዳሩንም የአዲስ አበባውንም ስዕሎች የሰራሁት እኔ ነኝ፡፡ አሁን ይህ ስራ አድካሚና እልህ አስጨራሽ ነው፡፡ 20 ሜትር በ7 ሜትር ስዕል መሳል ከባድ ነው፡፡ ከዚያ ይልቅ ትንንሽ ብዙ ስዕሎችን መስራት ይቀላል፡፡ እኔ የማስበው ያሉኝን ነገሮች ተጠቅሜ፣ ሙያዬን ወደ ገንዘብ መቀየርና ከአንድ አቅጣጫ ጠባቂነት ራሴን ማውጣት ነው፡፡ በዚህ በኩል እድለኛ ነኝ፤ ፈጣሪ እረድቶኛል፡፡ ለምሳሌ “አርት ቴራፒ” በሚል ለጋምቢ ሆስፒታል ፕሮፖዛል አስገብቼ መልስ እየጠበቅኩ ነው፡፡
“አርት ቴራፒ” ምንድን ነው?
አንድ ታማሚ በተኛበት የሆስፒታል ክፍል ፊት ለፊቱ አንድ ማራኪ ስዕል ቢሰቀል፣ ያንን ስዕል በማየትና በመመራመር፣ ህመሙን ለአፍታ ያህል ቢረሳ ቀላል አይደለም፤ የጎንዮሽ ጉዳት የሌለው መድሀኒት ነው፤ ስለዚህ በዚህ መልኩ ስዕሎችን ሰርቼ ህመምተኞች ክፍል ለመስቀል ምክረ ሀሳብ ባህርዳር ለሚገኘው ጋምቢ ሆስፒታል አቅርቤያለሁ። ምን ለማለት ነው… ያሉትን አማራጮች ሁሉ እሞክራለሁ፤ ከማንኳኳቸው 10 በሮች አንዱ ይከፈታል፡፡
በአሁኑ ወቅት በጉራማይሌ አርት ጋለሪ “ነቁጥ” የተሰኘ የስዕል አውደ ርዕይ ለዕይታ አቅርበሃል፡፡ ስራዎችህ ሁሉ የተሰሩት ደግሞ በከብት ቆዳ ላይ ነው። የስዕል (art) ፍልስፍናህ ምንድን ነው?
እንግዲህ የእኔ አርት ፍልስፍና የምለው ገና በሂደት ላይ እንዳለ ይሰማኛል፡፡ እኔ እንደ ትልቅ ነገር የማነሳው፣ በዚህኛው በ“ነቁጥ” ብቻም ሳይሆን ከመጀመሪያው አንስቶ በነበሩ ሥራዎቼ ጎልቶ የሚታይ ነገር አለ፡፡ “ተቃርኖን ማስታረቅ” የሚል ነው፡፡ ሁለት በሀሳብ፣ በቅርፅና በቀለም የሚለያዩ ነገሮች አንድ ላይ የሚሆኑበት ክፍል ፈልጎ፣ የማቀራረብና ማስታረቅ አካሄድ ነው። ለምሳሌ ኢትዮጵያ የምትባለው አገር በአስደማሚ ተቃርኖዎች የተሞላች፤ ነገር ግን ተቃርኖዎቿ ጌጥ የሆኑላት አገር ናት፡፡ ለአብነትም ዳሎል በጣም የአገሪቱ ዝቅተኛ ቦታ ነው፣ ራስ ዳሽን ከአፍሪካ በከፍታው ሁለተኛ ደረጃ  ላይ የሚገኝ ትልቅ ተራራ ነው፡፡ ሁለቱ በአንድ አገር በጣም በተቃርኖ ደግሞም ውበት ሆነው ተቀምጠዋል፡፡
ለእኔ ምዕራባዊ የሆነው አጠቃላይ ፍልስፍና “ትራዲሽናል” ሲል ያስቀኛል፡፡ ዘመናዊነት (ሞደርኒቲ) የባህላዊ ሂደቶች ቅጥያ ነው እንጂ በተለየ ሁኔታ የተፈጠረ አይደለም፡፡ ቀደም ብሎ የነበረው ባህላዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ሂደት ቀስ በቀስ እየተቀየረ ይሄዳል እንጂ በአንዴ ብጥስ ብሎና ከባህላዊነቱ ተለይቶ ብቻውን የቆመ አይደለም፡፡ ስለዚህ ዘመናዊነት ራሱን ለማስቀጠል አሁንም ባህላዊነት የግድ ያስፈልጋል፡፡ እኔ በስራዬ በአብዛኛው ባህላዊ ኤለመንቶችን እወስዳለሁ። በዚያው ልክ በጣም ዘመናዊዎቹንም እወስድና በጣም አስታርቄ አንድ የተጣጣመና የተቀናጀ ነገር እፈጥራለሁ። ብዙ ስራዎቼ ላይ የሚታይ ባህርይ ነው፡፡ ፈጣሪ በስራዎቹ ላይ የገለፀውም ይህንን ውበት ይመስለኛል፡፡ ይሄ ነገር ነው እንዳይሰለቸን የሚያደርገው፡፡ አሁን ቅጠል አንድ አይነት ተመሳስሎ ይኖረውና በዚያ ውስጥ ልዩነት አለው። ፋብሪኬትድ የሆነ ወይም ሰው የሰራው ነገር ነው ቶሎ የሚሰለቸው፡፡ ይሄ ከፈጣሪ የወሰድኩት ትልቅ ጥበብ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ሰው ሁሉ በፈጣሪ ሊነቃቃ ይችላል፡፡ በተፈጥሮ ብቻ ወይም በተለያየ ነገር ሊነቃቃም ይችላል፡፡ እኔ በራሱ በፈጣሪ ነው የተነቃቃሁት፡፡ እንደ አምላክ ከማምለክ በዘለለ  እንደሚጠበብ ሰው “creative-personality” አድናቂው ነኝ፡፡
“ነቁጥ” በሚል በሰየምከው  አውደ ርዕይህ ላይ ስራዎችህ ለምንድን ነው በከብት ቆዳ የተሰሩት? “ነቁጥ” ስትል የሰየምከውስ በምን ምክንያት ነው?
እኔ ወደ ቆዳ አርት የገባሁት መጀመሪያ እንደ አንድ ገጠር እንደተወለደ ልጅ፣ ከበሬና ላም ጋር ያለኝ ግንኙነትና ቅርበት የጠበቀ ነው፡፡ እንደውም አያቴ ስታሳድገኝ “ትርባልኝ” የምትባል ላም ነበረች፤ለእኔ ብቻ የተመደበች፡፡ ቀጥታ አፌን ከፍቼ፣ አያቴ ወተት አፌ ላይ እደረገች ነው ያሳደገችኝ፡፡ ከዚህ አለፍ ብዬ በሬን መመልከት ጀመርኩ፡፡ በሬ እየተገረፈ አርሶ ያበላል፣ ከዚያ ስጋውን ይሰጣል፡፡ ቆዳውን ለገመና መሸፈኛ ይሰጣል፡፡
በመፅሐፍ ቅዱስ አማኒያን ዘንድ ለመጀመሪያ ጊዜ ሰው በሀጢያቱ ምክንያት ፀጋውን ተገፍፎ፣ ራቁቱን ሲቀር ገመናው ለመሸፈን የተጠቀመው ቅጠል ነው። ነገር ግን ቅጠል ረጅም ጊዜ ስለማይቆይ ጌታ ራሱ ቆዳ ነው የሰጣቸው፤“ለምድ አለበሳቸው” ይላል፡፡ ቀንዱን ለመጠጫ፣ ጅራቱን ለመግረፊያ እንጠቀማለን፡፡ በፖለቲካዊ አንድምታም ከሄድን፣ ነጋሪት ተጎስሞ አዋጅ የሚነገረው ከበሬ ቆዳ ተሰርቶ ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ እበቱ ራሱ ማገዶ ይሆናል፡፡
በሬ ቁርጥምጥም አድርገን የምንጠቀመው ፍጥረት ነው፡፡ ለዚህ ሁሉ ፈቃደኛ የሆነም ነው፡፡ ይህ ነው መነሻዬ፤ ቆዳ ላይ ያተኮርኩበት፡፡ በሬ ያ ሁሉ ቆዳው ላይ ያለ ዥንጉርጉር፣ ትልቅም ይሁን ትንሽ ነቁጥ፣ ብዙ በሬ አያደርገውም፤ እነዛ ተባብረው ነው በሬ የሚያሰኙት፡፡ ይህ እሳቤ የበለጠ ስለሳበኝ ነው ያተኮርኩበት፡፡
በተለይ በገጠር አካባቢ ቆዳ ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ነው ያለው---
እውነት ነው፡፡ የገጠሩ የቆዳ አጠቃቀም ከተነሳ አይቀር በጣም የሳበኝ፣ አጎዛውን ግድግዳ ላይ ሰቅለው፣ ለጌጥና ለአይን ማረፊያ ያደርጉታል፡፡ ከዚያ ያወርዱና አንጥፈው ይተኙበታል፡፡ ሲተኙ ደግሞ ያሸትቱታል፡፡ እነዚህ የውበት ልምምዶች ሁለት አይነት ነገር አላቸው፤ ተግባራዊም ውበታዊም። እነዚህን ሁለት መልክ ያላቸው ስራዎች ለእይታ ማቅረብ በምዕራባዊያን አረዳድ፤ “ማቴሪያል ካልቸር” ነው የሚሉት፡፡ ምን ማለት ነው? ሰው ለዕለት ተዕለት ኑሮው የሚጠቀምባቸው እንጂ የተጠበበት አርት አይመስላቸውም፡፡ እንደኔ እምነት ግን ሙዚየም ባለማቅረባቸው እንጂ እነዚህ ስራዎች በምዕራባዊያን ሙዚየሞች ከሚታዩ ስዕሎች በላይ ጠንካራ ናቸው፡፡
እንደውም አሁን በዘመናዊ ስነ-ጥበብ ትልቁና ጠንካራ መሆን አለበት የሚባለው አርቲስቱ በአይን ታይቶ ከሚያበቃና ዋው ከሚያስብል ስራ በዘለለ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የሆኑ ጉዳዮችን የሚያነሳ፣ የሚቀሰቅስና የሚታገል ነው። እነዚህ አርቲስቶች ከእለት ተእለት ህይወታቸው ጋር የተቆራኙ ነገሮችን ወስደው ለታይታና ለእይታ ብለው ሳይሆን ከልብ የመነጨ ሀሳባቸውን ያንጸባርቁባቸዋል፡፡ ለነዚህ ስራዎች ደግሞ ቦታ ተሰጥቶ መካተት አለባቸው የሚል ሀሳብ ይዤ  ነው የተነሳሁት፡፡
ታዲያ ስራዎችህ ተቀባይነት አግኝተውልሃል?
አሁን ይሄን የሚደግፉልኝ ሱዛን ፎግል፣ ካሮል ዳንከል እና ሌሎችም ፀሀፊዎች አሉ፡፡ እነዚህ ፀሀፊዎች የአፍሪካዊያን አርት በምዕራባዊያን ሙዚየም ለእይታ ሲቀርብ እንደ እቃ ነው የሚከለኮለው እንጂ እንደ ሪፋይን አርት በስርዓቱና በክብር አያቀርቡትም፡፡ የራሳቸውን ግን ከአምላክና ከሰማይ የወረደ አድርገሽ እንድትመለከቺው፣ ያንን ስሜት ይፈጥሩብሻል፡፡ እኔ እንደምታዪው፤ እነዚህን ሞሰቦች፣ አገልግሎችና ሌሎች እቃዎችን ከእቃነት በዘለለ ራሳቸው ጥልቅ የሆነ ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ እሳቤ ያላቸው መሆኑን ለማሳየት ሞክሬያለሁ፡፡ ቅድም የጠቀስኩልሽ ፀሀፊዎች፣ይህንን ስራና አስተሳሰብ ይደግፉታል፤ተቀባይነቱ የሚያጠራጥር አይደለም፡፡
በአውደ ርዕዩ ላይ ከቀረቡት መካከል የገረመኝ፣ ትልቁ በቆዳ የተለበጠው መሶብ፣ በቁልፍ ተቆልፎ በርካታ የቁልፍ መክፈቻዎች ከበውታል፡፡ እስቲ የዚህን መሶብና የቁልፍ መክፈቻዎቹን ምስጢር አብራራልኝ?
በዚህ መሶብና በቁልፉ ማስተላለፍ የፈለግኩት እንጀራ፣ ተስፋና ዕድልን ነው፡፡ የእቃዎቹን አቀራረብ installation (ኩልኩል) እንለዋለን። ጥልቅ የሆነውን የሰው ህይወትና በሕይወቱ የሚገጥሙትን ጉዳዮች ሊገልፅ በሚችል መንገድ የምናስቀምጥበት ነው:: ሰው ተስፋ አለው፣ ዕድልም አለው፣ እንጀራም አለው፡፡ ተስፋው ያለ ማቋረጥ ይሄንን ቁልፍ ለመክፈት እንዲሞክር ያደርገዋል። ዕድሉ ሙከራውን ያሳካለታል፡፡ እንጀራው በነዚህ ሂደቶች የሚገኝ ስኬት ነው፡፡ ይህ የተቆለፈ መሶብ በስሩ ከተደረደሩት መዓት ቁልፎች አንዱ ይከፍተዋል። የሚከፍተው ቁልፍ ምንም ምልክት የለውም፡፡ ይሄ የብዙ ሰዎችን ሀሳብ ይሞግታል፡፡
በምን መልኩ?
ቁልፉ ከእነዚህ ቁልፎች መሀል እንዳለ እናውቃለን። የሰው ልጅ ከእነ ዕድሉ፣ ከእነ ስጦታው ነው የተፈጠረው፤ ነገር ግን አብዛኛው የሚሞክርና የሚጥር አይደለም፡፡ አንድ ሰው ተስፋ ካደረገ፣ ከጣረ ዕድሉ ቁልፉን እንዲያገኝ ያደርገዋል። ይሄ ሙግት በውስጥሽ መመላለሱ አይቀርም፡፡
ለጉብኝት የሚመጡ ሰዎችን የዚህን ሞሰብ ቁልፍ ሞክረው እንዲያገኙ ስትጋብዝ አይቻለሁ። እኔም በርካታ ቁልፎችን ሞክሬ መሶቡን መክፈት አልቻልኩም፡፡ ለመሆኑ እስካሁን ሞክሮ የተሳካለትና የከፈተው አለ?
የሚገርምሽ አንድ ልጅ ሞክሮ ተሳክቶለታል፡፡ በውስጡ ምን አገኘ የሚለውን አሁን አልናገረም፤ ነገር ግን ይሄ ልጅ መክፈት አለብኝ ብሎ ቆርጦና ወስኖ ነው የተቀመጠው፡፡ ልጁ ምን ያህል ሰዓት  ታግሶ ወስኖ እንደተቀመጠ ስመለከት፣ የልጁ ቁርጠኝነት ለብዙ ሰው ትምህርት የሚሆን ነው። ህፃናትም በብዙ ትዕግስት ፈልገው ፈልገው፣ “እባካችሁ የትኛው ነው፣ አሳዩን?” እስከ ማለት ደርሰዋል፡፡
አንተ ግን ቁልፉ የትኛው እንደሆነ ታውቀዋለህ?
በፍፁም! እኔም አላውቀውም፡፡ አንድም የሌላው ህብረተሰብ አካል ለመሆን፣ በሌላም በኩል ለራሴ እንዳላዳላ በሚል አላውቀውም፡፡ እንግዲህ በምዕራቡ ዓለም ስዕል በእጅ አይነካም፤ አይዳሰስም፤ በቃ ሀይማኖታዊ ነገር አድርገው ነው የሚያስቀምጡት። አምስት ሜትር ከስዕሉ ርቀሽ ነው የምትመለከቺው። እኛ ጋ ትነኪዋለሽ፣ ትዳስሺዋለሽ፣ የሰቀልሺውን ራሱ አውርደሽ ትተኚበታለሽ፤ ስለዚህ የሚዳሰስ የሚታይና የሚሸተት ሥራ ነው የምንሰራው፡፡
አውደ ርዕዩን ብዙ የውጭ ዜጎች ሲጎበኙት ተመልክቻለሁ፡፡ ጎብኝዎች የሰጡህ አስተያየት ምን ይመስላል?
ያገኘኋቸው ሁሉ በጣም ፍላጎት ያሳደረባቸው ነገር ምን መሰለሽ? ወይ ዘመናዊነቱ ውስጥ ጥልቅ ብለህ አልገባህ ወይ በጣም ባህላዊ በሚባል መንገድ አልመጣህ፤ ሁለቱን አቻችለህ ስለምትሞግተን እኛም የሀሳብ ለውጥ ለማድረግ ተመችቶናል፡፡ በሌላ በኩል በአይን ከመታየት አልፎ እንድንነካ፣ አገላብጠን እንድናይ ዕድል አግኝተናል፡፡ የሚዳሰስ የሚሸተት የሚታይ ስዕል ማየታችን አዲስ ስሜት ፈጥሮብናል ሲሉ  ተናግረዋል፡፡
ሌላ መናገር የምፈልገው ነገር፣ በምዕራባዊያን ፕላት ፎርም ውስጥ የተካተተው የስነ- ጥበብ ፍልስፍና እና ታሪክ የሌላውን አለም ያላቀፈ ነው የሚል ሙግት አለ። እነ ፒካሶ በተነሱበት ዘመን በተጓዳኝ በአፍሪካ፣ በላቲን አሜሪካ፣ ከምዕራቡ ተመጣጣኝ የሆኑ የአርት ክንውኖች የነበሩ ቢሆንም የተካተተው የምዕራቡ ብቻ ነው የሚል የሀሳብ ፍጭት ስላለ፣ በዚያ ሙግት ውስጥ የእኔን ትንሽ ነፀብራቅ ለማሳየት ነው እየሞከርኩ ያለሁት፡፡
በስዕሎቹ በቆዳ የተለበጠ ቴሌቪዥን ተመልክቻለሁ። ትርጉሙ ምንድን ነው?
ቴሌቪዥን በአገራችን የማህበረሰብን ስትራክቸር የቀየረ ነው፡፡ ምን ማለት ነው--- ቀደም ባለው ጊዜ ቤት ውስጥ ስንቀመጥ፣ ትልልቅ ሰዎችን ከብበን ነበር፡፡ ማዕከል የሚሆኑት እናት አባቶቻችን ናቸው። አሁን ደግሞ ቴሌቪዥን ከበን ነው የምንቀመጠው፡፡ የቴሌቪዥኑ አቀማመጥ ደግሞ ለሁሉም ለህፃን ለአዋቂው እንዲመች ተደርጎ ነው የሚዘጋጀው፡፡ ዱሮ ተረት፣ ምክር የምንሰማው ከታላላቆቻችን የሚጠቅመንን ብቻ ነበር፡፡ አሁን ቴሌቪዥን የምናየው ያለ ዕድሜ ገደብ ነው፡፡ ለልጅ ነው ለአዋቂ ነው የለም፣ ያውም ተገምግሞ በማያልፍ የትኛውም ሀሳብ ውስጥ አብረን እንሰለፋለን፡፡ ይሄ ለእኔ አስጊ ነው፡፡ ቴሌቪዥኑን ቆዳ ያለበስኩት፣ ከቴሊቪዥኑ የሚወጣውን እኛ ብናስተካክለውና ብንዋጀው የሚል ምኞቴን ለማስተላለፍና የሚጠቅመንን ብቻ የምንሰማበት ልናደርገው ብንችል የሚለውን ህልሜን ለማሳየት ነው፡፡ እንግዲህ የሀሳብ ተቃርኖውን የሚያሳይ ነው። ቆዳው የእኛ ነው፤ ቴክኖሎጂው የእነሱ ነው። ይሄ በእጄ የያዝኩት ስልክ ጥሩም መጥፎም አይደለም፤ በስልኩ የምጠቀምበት ነገር ነው ጥሩና መጥፎ ሊያሰኘው የሚችለው፡፡ በስልኩ ደውዬ “ሰው ግደል ወይም የወደቀ ሰው አንሳ” ስል ውጤቱ ይወሰናል ማለት ነው፡፡
አሁን ደግሞ በአሜሪካ ስላሳየኸው አውደ ርዕይ  እና በቅርቡ በግብፅና በኢኳዶር ስለምታሳየው የስዕል አውደ ርዕይ አጫውተኝ ----
ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ፣ አንድም ቀን ታዋቂ ለመሆን ብዬ ከአርት ጋር ተቆራኝቼ አላውቅም፤ ነገር  ግን በፍቅርና በፍላጎት ተሞልተሽ ስትሰሪ፣ አይን ውስጥ ትገቢያለሽ፡፡ በመጀመሪያ ያገኘሁት እድል በአሜሪካ ላስቬጋስ በኔቫዳ ዩኒቨርሲቲ የሚገኝ የስነ-ጥበብ ተቋም ነው፡፡ በማይመች አካባቢ ውስጥ ሆኜ በባህርዳር ለአምስት ዓመታት ሥነ-ጥበብ ላይ በመስራቴ በተለይም ከወጣሁበት አካባቢ ሀይለኛ ግንነት ያለው ስራ መፍጠር በሚል “ፐብሊክ ሌክቸር” ሳደርግ፣ በተጨማሪም ስራዎቼን “ባሪክ” ሙዚየም ውስጥ ከንግግሬ ጎን ለጎን ለእይታ አቅርቤ ነበር፡፡ ከዚያም ለሶስት ሳምንታት ያህል ግራንት ሆል ጋለሪ ሆል ውስጥ ስራዎቼ ለእይታ በቁ፡፡ ቦልደርሲቲ በሚባል ከተማም ስራዎቼ ለህዝብ ለእይታ በቁ፡፡ በዚያው ከተማም ለህዝብ ንግግር አድርጌአለሁ። ይሄ በጣም ያስደሰተኝ ኢትዮጵያን የማያውቁ ሰዎች ገጥመውኝ ነበር፡፡ በእኔ ስራ ምክንያት ኢትዮጵያን ማወቃቸው ትልቅ ደስታ ፈጥሮብኛል፡፡ እነ ኃይሌ ገ/ሥላሴን እያወቁ ኢትዮጵያን አያውቁም፡፡ ለእነዚህ ሰዎች ስለ ኢትዮጵያ መናገሬ ያስደስተኛል። እርግጥ ነው ስሄድ አበባ ይዞ የተቀበለኝ የለም፤ የሰራኋቸውን ለእይታ ያቀረብኳቸውን ስራዎቼን ብዙ ግምት ውስጥ ያስገባ የለም፤ ሆኖም ኢትዮጵያን አስተዋውቄያለሁ፡፡ እርግጥ ሲጠሩኝ ከወጣሁበት አካባቢና ባህል ጋር የተቆራኘ ሥራ በመስራቴ ሁኔታዎች በማያበረታቱበት ድባብ፣ በፈተና ውስጥ ያለማቋረጥ የስዕል አውደ ርዕይ ለአምስት ዓመት በማቅረቤ ነው፡፡ በባህርዳር በቆየሁባቸው በነዚህ ጊዜያት አመታዊ አውደ ርዕዮች እንዲኖሩ አድርጌያለሁ፡፡
ሁለቱ ላይ በተለይ የአዲስ አበባ አርቲስቶች እንዲሳተፉ በማድረግ፣ ባህርዳርን አማራጭ የስነ-ጥበብ ማዕከል የማድረግ ህልሜን ለማሳካት ሙከራዬን የጀመርኩበት ነው፡፡ “ጥበበ ባህርዳር” “አርት ኦፍ ዘ ናይል” በተሰኙ ኤግዚቢሽኖች ነው ይህን የሰራሁት። በኋላም በግሌ ሦስት ኤግዚቢሽኖች አቅርቤያለሁ፡፡ በብሔራዊ ሙዚየምም “ሀገረ ቀለም ኢትዮጵያ” የተሰኘ በሀሳብም፣ በቴክኒክም ሆነ በቀለም በዛና ተለቅ ያለ ኤግዚቢሽን ነበረኝ። አሁን በሶሻል ሚዲያም በርትቼ እየሰራሁ ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎችም በኔ ተነቃቅተው እየፃፉ ይገኛሉ። ናይጄሪያ በሚታተም “ታይምስ” የተሰኘ መፅሄት ላይ “ዘ አርቲስት ኦፍ ናሽናል ኮንሺየስነስ” በሚል ርዕስ ሽፋን አግኝቻለሁ፡፡
በግብፅና በኢኳዶር ስለምታቀርበው አውደ ርዕይ ንገረኝ---?
በኢኳዶር የሚካሄደው ዓለም አቀፍ ሰሚት ነው። በግብፅ ደግሞ “ኢንተርናሽናል አርት ሲምፖዚየም” ከአፕሪል 12 እስከ 24 ቀን 2018 ይካሄዳል፡፡ በዚያ ላይ እሳተፋለሁ፡፡ በዚህ ሁሉ ደስኛ ነኝ፡፡ አገራችን የ3 ሺህ ዓመት ታሪክ ያላትና የባህልና ታሪክ አገር መሆኗ፣ ለአንድ የፈጠራ ሰው በተለይ በስነ-ጥበብ ሙያ ውስጥ ላለ ሰው እድለኝነት ነው፡፡ ብዙ የምንሰራበት እድል አለ፡፡ ህልሜ ስዕልን ለእይታ አቅርቦ ከመሸጥ በዘለለ ጠንካራ ንቅናቄ ለመፍጠር ነው፡፡ ይህ ደግሞ ይሳካል፡፡