Administrator

Administrator

          የአዲስ አበባ ከተማን የትራንስፖርት ችግር እንደሚፈታ የተነገረለት ሸገር የከተማ አውቶቡስ ትናንት ስራ የጀመረ ሲሆን ለአንድ አውቶቡስ 3.61 ሚ. ብር ፣ ለ50 አውቶብሶች 180 ሚ. ብር ወጪ መደረጉ ታውቋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የትራንስፖርት ፕሮግራሞች ማስተባበሪያ ጽ/ቤት፣ ብረታ ብረት ኢንጂነሪግ ኮርፖሬሽን እንዲሰራለት ካዘዛቸው 300 አውቶቡሶች ውስጥ 50ዎቹን ተረክቦ ሥራ
ማስጀመሩን የአስተዳደሩ የትራንስፖርት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት ካፓሲቲ ኦፕሬሽን መምሪያ ኃላፊ
አቶ ሙሉቀን አማረ ገልጸዋል፡፡ አውቶብሶቹ ከአንድ ኪሎ ሜትር በታች የሚቆሙ ስላልሆነ፣ የረዥም ርቀት ፍላጎት የሚያሟሉ ናቸው ያሉት አቶ ሙሉቀን፤ ታሪፋቸውም ኪስ አይጎዳውም ብለዋል፡፡ እስከ 4 ኪሎ ሜትር 1.50፣ ከ4-6 ኪ.ሜ 2 ብር፣ ከ6-9 ኪ.ሜ 3 ብር፣ እስከ 10 ኪሎ ሜትር ርቀት 3.50 እንደሚያስከፍሉ በመግለፅ፡፡ አውቶብሶቹ ለጊዜው የሚጓዙባቸውና የተመረጡ መስመሮች፡- ከሜክሲኮ ቦሌ፣ ከቦሌ ፒያሳ፣ ከፒያሳ መገናኛ፣ ከሜክሲኮ ዓለም ባንክ፣ ከሳሪስ አቦ መገናኛ እንደሆኑ የጠቀሱት ኃላፊው፤ ከ3ወር በኋላ 150 አውቶብሶች ሲረከቡ የመስመሮቹ ቁጥር 21 እንደሚደርስና የቀሩትን አውቶቡሶች አጠናቀው አጠናቀቁ ሲረከቡ እንደየአስፈላጊነቱ ሌሎች መስመሮች እንደሚከፈቱ አስረድተዋል፡፡ ሸገር አውቶቡስ የተቋቋመበት ሦስት መሰረታዊ ነገሮች አሉት ያሉት ኃላፊው፣ በአንድ ኪ.ሜ የሚቆም መደበኛ አገልግሎት፣ የተማሪዎች የትራንስፖርት አገልግሎትና ፈጣን የትራንስፖርት
አገልግሎት (ከአስኮ እስከ ጀሞ (16 ኪ.ሜ) እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ሸገር አውቶቡስና አንበሳ አውቶቡስ ሁለቱም የመንግስት የልማት ድርጅቶች ስለሆኑ ጎን ለጎን ይሰራሉ ያሉት አቶ ሙሉቀን፤ አንበሳ አውቶቡስ 814 አውቶቡሶች፣ ሲቪል ሰርቪስ ወደ 400 አውቶቡሶች፣ ሸገር ደግሞ 300 አውቶቡሶች ይኖሩታል፣ ሆኖም ጥናቶች፤ የከተማዋ የትራንስፖርት ፍላጎት በአማካይ 3500 አውቶቡሶች እንደሆነ የሚያመለክቱ ስለሆነ ሌሎች ተጨማሪ አውቶቡሶች ያስፈልጋሉ ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት አውቶቡስ ለመጠበቅ ከአንድ ሰዓት በላይ መጠበቅ ያስፈልጋል ያሉት ኃላፊው፤ የሸገር አውቶቡሶችን በ10 ደቂቃ ውስጥ ማግኘት እንደሚቻል ቢገልፁም በምን መንገድ እንደሆነ አልገለፁም፡፡ የሸገር ዘመናዊ አውቶቡሶች የደህንነት ካሜራ የተገጠመላቸው ሲሆን፣ አውቶብሶቹ የት እንዳሉ መቆጣጠር የሚያስችል ጂፒኤስ፣ የአየር መቆጣጠሪያ ኤሲ እንዳላቸውና፣ አውቶማቲክ ትኬት እንደሚጠቀሙ ሃላፊው ተናግረዋል፡፡

አንድ ተኩላ አንዲት የበግ ግልገል፣ ከዕለታት አንድ ቀን አግኝቶ በጣም አስጐመዠችው፡፡ እንዲሁ
እንይበላት ምክንያት ያስፈልጋል ብሎ አሰበ፡፡ ስለዚህ አንዳንድ ጥያቄና ወቀሳ መሰንዘር ጀመረ፡፡
“አንቺ’ኮ ባለፈው ዓመት ሰድበሽኛል፤ ታስታውሻለሽ?”
ግልገሊትም፤
“ኧረ በጭራሽ ጌታ ተኩላ፤ እኔ አምና አልተወለድኩም”
ጌታ ተኩላ፤
“አንቺ ቀጣፊ! እንዲያውም በኔ መስክ ላይ እየተዘዋወርሽ ትግጪ ነበረ፡፡”
ግልገሊት፤
“ኧረ እኔ ገና ሣር ለመብላት ያልደረስኩኝ ጨቅላ ነኝ፡፡ ጥርሴም አልጠነከረም’ኮ!”
ጌታ ተኩላ፤ ድምፁ እየሻከረና ቁጣ ቁጣ እያለው መጣ፡-
“እንግዲያው ውነቱን ልንገርሽ፣ አዲስ ከፈለቀው ኩሬዬ ውሃ ስትጠጪ ታይተሻል፡፡ ጥግብ ብለሽም
በአካባቢው ፈንጭተሻል!”
ግልገሊትም፤
“ጌታ ተኩላ፤ እኔ ፈፅሞ ውሃ ጠጥቼ አላውቅም፡፡ ገና የእናቴን ጡት ጠጥቼ ያልጠገብኩ አንድ ፍሬ
ግልገል ነኝ!”
ጌታ ተኩላም፤
“ልታጭበረብሪኝ አትሞክሪ! እኔ ደጋ ወጥቼ፣ ቆላ ወርጄ ያጠራቀምኩትን ሥጋ በልተሽብኛል!”
ግልገል፤
“ጌታ ተኩላ! እንዴት መግባባት እንዳቃተን አልገባኝም፡፡ እኔ’ኮ በግ ነኝ፡፡ በግ ሥጋ አይበላም፡፡
ደሞም ከአንተ መኖሪያ ዋሻ ገብቼም አላውቅም፡፡ በቅጡ ተረዳኝ እንጂ እንግባባ”
ጌታ ተኩላም በጣም ተቆጥቶ፤
ያ “ለመግባባታችን ዋና ምክንያትማ የእኔ ረሀብ ነው”
ግልገልም፤
“እኛ ውይይት ውስጥ ያንተን ረሃብ ምን አገባው?” ስትል በጥሞና ጠየቀችው፡፡
ጌታ ተኩላ፤
“አየሽ፣ ያንቺ ችግር ይሄ ነው፡፡ አርቀሽ አታስተውይም፡፡ እኔ ተኩላ፤ ሰማይ ዝቅ መሬት ከፍ ቢል
እራቴን ሳልበላ ማደር የለብኝም!”
ግልገሊትም፤
“እሱ ልክ ነው፡፡ ግን ዕቅድህን ሳታሳውቅ (ፕሮፖዛል ሳታቀርብ)…” ብላ ሃሳቧን ተናግራ
ሳትጨርስ፣ ጌታ ተኩላ እንደ ጉድ ተስፈንጥሮ ግልገሊት ላይ ሰፈረባት፡፡
አንዲትም አጥንት ሳትቀረው ቆረጣጥሞ እራቱን በላ!
(እነሆ ግልገሊት፤ “ሳታመሃኝ ብላኝ” የተሰኘውን ምርጥ የአማርኛ ተረት ባለማወቋ፣ ጉዳዬን
አስረዳለሁ ብላ ስትዳክር ተበላችና አረፈችው!”)
    ***
ችግርን በአግባቡ በውይይት መፍታት የሠለጠነ መንገድ ነው፡፡ ሆኖም ይህ ሊሆን የሚችለው ሁለቱም ተወያይ ወገኖች ከጀርባ የተደበቀ ዓላማ (አጀንዳ) የሌላቸው እንደሆነ ነው፡፡ በአብዛኛው የአገራችን ሰው፣ ቡድን ወይም ፓርቲ የተደበቀ አጀንዳ በሆዱ ይዞ በመወያየቱ ምክንያት ውይይቶች ችግርን የመፍታት አቅም የላቸውም፡፡ ተወያዮቹ የመቀራረቢያ ምክንያት ፍለጋ ሳይሆን የመበላላት ሰበብ ፍለጋ ነው የሚሄዱት፡፡ If you are in the business of duck – hunting, you go where the ducks are. (God
is back: Exporting America’s God ከሚለው መጽሐፍ) ይላሉ ፈረንጆቹ፡፡ ወደምታድነው
እንስሳ ሂድ ነው ነገሩ፡፡ ዳክዬ አዳኝ ከሆንክ ዳክዬ ወዳለበት ሂድ እንደማለት ነው፡፡
ለጉዳይህ መፍትሔ የምታገኘው ጉዳይህ ወዳለበት በመሄድ ነው ማለትም ነው፡፡ አደን ሄደህ
ውይይት ምን ይፈይዳል? ማለትም ነው፡፡
ለየጉዳዩ ሰበብ ከጀርባ እየቋጠረች አገራችን ዛሬ እደረሰችበት ደርሳለች፡፡ በንጉሡ ዘመን፤ በደርግ
ዘመንና አሁንም መጠኑ ይለያይ እንጂ፤ ወይ በእጅ አዙር መነጋገር፣ ወይ በድብቅ አጀንዳ መተጋተግ አሊያም ተቀናቃኝን ጥርስ ውስጥ ማስገባት፤ ከልማድም አልፎ ባህል የማድረግን ሁኔታ ለዓመታት ስንታዘብ ኖረናል፡፡ ትዕግሥቱን ሰጥቶንና “ተመስገን ይሄንንም አታሳጣን!” እያልን እዚህ ደርሰናል፡፡
“ተመስገን ይለዋል፣ ሰው ባያሌው ታሞ
ካማረሩትማ ይጨምራል ደሞ!”
ይሏል ይሄው ነው፡፡ በበገናና ዘለሰኛ ሲሆን ይበልጥ በለሆሣሥ ይሰማል፡፡ ተመስገን ከማለት አልፈን፣ አዕምሮአችንን አንቅተን፣ ችግሮቻችንን አይተን፣ መፍትሔዎቻችንን ሸተን፣ አገራችንን አገር ለማድረግ አንዱ ቁልፍ ነገር በለውጥ ማመን ነው፡፡ ግትር አለመሆን ነው፡፡ እኔ ያልኩት ብቻ ነው ከሚል የአስተሳሰብ ጋግርት መላቀቅ ነው፡፡ ስለሠራነው ሥራ አለመኮፈስ ነው፡፡ ስለቀረንና፤ ድክመታችን ነው ወደምንለው፤ መሄድ ነው፡፡ እንደ አጭበርባሪ ነጋዴ “ባመጣሁበት ውሰደው” ማለትን መተው ነው፡፡ ስንጥቅ ማትረፋችን የታወቀ ነውና እንዳያስተዛዝበን ነው፡፡ ዛሬ የሃያ አምስት ዓመት ጉዟችንን ስናወሳ ለመሞጋገስ ብቻ መዘጋጀት የለብንም፡፡ ገጣሚ ፀጋዬ ገብረመድህን እንደሚለው፤
“ጅላጅል ምላስ ብቻ ናት፣
ማሞካሸት የማይደክማት
ቀን አዝላ ማታ እምታወርድ
ንፉግን ልመና እምትሰድ”
ከውዳሴው ባሻገር ራሳችንን መጠየቅ ያሻል፡፡ አንድ ፀሐፊ እንዳለው፤ “እስከዛሬ የሆነው ሁሉ ለዚህ
ቀን ዝግጅት ነበር፡፡ ይሄኛው ቀን ደግሞ ለነገው መዘጋጃ ነው” (all that has gone before was
a preparation to this day, and this, only a preparation to what is to come)
ዲሞክራሲ የት ደረሰ? የፖለቲካ አመለካከት ልዩነት ጠበበ ወይስ ሰፋ? የኢኮኖሚ ዕድገታችን ምን ውጤት አመጣ? ብዙዎች እየማቀቁ ጥቂቶች እየመጠቁ ያሉበት የሃብት ክፍፍል ነገ የት ያደርሰናል? የሕግ የበላይነት ዕውን ሆኗል? የሲቪክ ማህበረሰቦች ሚናቸውን እንዲወጡ ተገቢው ሁኔታ ተመቻችቶላቸዋልን? ከግንባር ወደ ፓርቲነትን የመቀየር ምኞታችን የት ደረሰ? ወደ ብሔራዊ መግባባት ለመድረስ ምን ያህል በቀናነት እየተጓዝን ነው? በዋናነነት ደግሞ ሙስናን የሙጥኝ ያለውን ሥርዓት እንዴት ልንገላገለው ነው? ከአመራር እስከ ምንዝር የተዘፈቀበት የሙስና አረንቋ፤ ዛሬ ሀ ብሎ እንቅፋቶቹን ማስወገድ የጀመረ ይመስላል፡፡ ዘግይቷል፡፡ ይሁን፡፡ ግን ገና ብዙ ይቀረዋል፡፡ በሥልጣን የባለጉትን አውርደን፤ ጨዋዎችን መተካት ነገ የሚጠብቀን ከባድ ተግባር ነው፡፡ የተመቻቸ የመቦጥቦጫ ክፍተት ዛሬም ሰፍቶ ተንሰራፍቶ እያለ፤ አዳዲስ ሹማምንት ብናስቀምጥ እዚያው ማጥ ውስጥ አዳዲስ ጥርስ እንደ መትከል ነው፡፡ ጓዳ ጐድጓዳው ተፈትሾ፣ ቀዳዳው ሁሉ መደፈን አለበት፡፡ አለበለዚያ ጋሞዎች እንደሚሉት፤ “ገመድ የምትበላው በቅሎዬ ብትሄድ፣ ልጓም (ብረት) የምትበላዋ መጣች” ይሆንና ለከፋ ብዝበዛ እንጋለጣለን!



 እስካሁን ከተሞከሩት የተሻለ ውጤታማ ነው ተብሏል
   ከዚህ በፊት ከተሞከሩት የኤችአይቪ/ ኤድስ መከላከያ ክትባቶች ሁሉ የተሻለ ውጤት አስገኝቷል የተባለ አዲስ ክትባት በመጪው ህዳር ወር ላይ በደቡብ አፍሪካ ሊሞከር እንደሆነ ኤንቢሲ ኒውስ ዘገበ፡፡ የኤችአይቪ/ኤድስ ኢንፌክሽንን በአንድ ሶስተኛ ያህል የመከላከል አቅም አለው የተባለው ይህ ክትባት በቀጣይ ሊደረግ በታሰበው ሙከራ የበለጠ ውጤታማ ይሆናል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ዘገባው፤ክትባቱ የሚሞከረው በ5ሺህ 400 ሰዎች ላይ እንደሚሆንም ገልጧል፡፡
ቫይረሱ በአለማቀፍ ደረጃ 35 ሚሊዮን ሰዎችን እንዳጠቃ የጠቆመው የኤንቢሲ ኒውስ ዘገባ፤በየአመቱ 1.2 ሚሊዮን ሰዎችን ለሞት እየዳረገ እንደሚገኝም አስረድቷል፡፡

Tuesday, 24 May 2016 08:29

የዘላለም ጥግ

- ድል አንድ ሺ አባቶች ሲኖሩት፤
ሽንፈት ግን ወላጅ አልባ ነው፡፡
ጆን ኤፍ.ኬኔዲ
- ድል፤ የዝግጁነትና የቁርጠኝነት
ልጅ ነው፡፡
ሳን ሃምፕተን
- ረዥም ዕድሜ ከኖርክ እያንዳንዱ
ድል ወደ ሽንፈት እንደሚለወጥ ታያለህ፡፡
ሳይሞን ዲ ቢዩቮይር
- ጠላት ባይኖር ትግል አይኖርም፡፡
ትግል ባይኖር ድል አይኖርም፡፡ ድል ባይኖር
ደግሞ ዘውድ አይኖርም፡፤
ቶማስ ካርሊሌ
- ከድል ጥቂት ነገሮችን ልትማር
ትችላለህ፡፡ ከሽንፈት ግን የማትማረው ነገር
የለም፡፡
ክሪስቲ ማቴውሶን
- በጦርነት ውስጥ ድልን የሚተካ
ምንም ነገር የለም፡፡
ዳግላስ ማክአርተር
- ድል ጣፋጭ የሚሆነው ሽንፈትን
ስታውቀው ነው፡፡
ማልኮም ፎርብስ
- ወደ ድል በሚደረግ ጉዞ
የመጀመሪያው እርምጃ ጠላትን መለየት ነው፡

ኮሪ ቴን ቡም
- ያለ ዕቅድ ጥቃት የለም፡፡ ያለ ጥቃት
ድል የለም፡፡
ኩርቲስ አርምስትሮንግ
- እውነተኛው ድል የዲሞክራሲና
የብዝኃነት ድል ነው፡፡
ሆስኒ ሙባረክ
- አሸንፋለሁ ብለህ ካሰብክ
ታሸንፋለህ፡፡ እምነት ድል ለማድረግ ወሳኝ
ነው፡፡
ዊሊያም ሃዝሊት
- ዲሞክራሲ፤ ዲሞክራት ያልሆነን
ቡድን ወደ ስልጣን ካመጣ፣ ያንን
የዲሞክራሲ ድል ልንለው እንችላለን?
ሪቻርድ ኢንጄል
- ድል ጣፋጭ የሚሆነው ያንተ
ወገን በማሸነፉ ነው - ወይስ የጠላት ወገን
በመሸነፉ?
ጆን ፓድሆሬትዝ
(ስለ ድል)



ይህ ጽሁፍ ሚያዝያ 21 ቀን 2008 ዓ.ም የአቶ አሰፋ ጫቦ ”የትዝታ ፈለግ” መጽሐፍ በጣይቱ የባሕልና ትምህርት ማዕከል አዳራሽ
በተመረቀበት ወቅት መጽሐፉን ለማስተዋወቅ ካደረግሁት ንግግር አጥሮና ተስተካክሎ (Edited) የቀረበ ነው፡፡

ዓለም ፀሐይ ወዳጆ
(Silver Spring, Maryland USA)

   የተወደዳችሁ እንግዶች፤ በቅድሚያ የዛሬው እንግዳችን አቶ አሰፋ ጫቦ ‹የትዝታ ፈለግ› በሚል ርዕስ ያሳተመውን መጽሐፍ ለምርቃት በማብቃቱ በጣይቱ የባህልና የትምህርት ማዕከል ስም ‹እንኳን ደስ አለህ!› እላለሁ::
በዛሬው ምሽት የትዝታ ፈለግ  በሚል ርዕስ ለንባብ ያበቃውን መጽሐፉን ልንመርቅ ነው የተሰባሰብነው:: መጽሐፉን በማነብበት ወቅት ብዙ ወደ ማውቃቸው ጊዜያትና ግለሰቦች የወሰደኝ ሲሆን የአጻጻፍ ውበቱም እጅግ አስደንቆኛል፤ የባህሪይ አቀራረፅ ችሎታውና የአካባቢ ስዕላዊ መግለጫውም አርክቶኛል::
አቶ አሰፋ ጫቦ፤ ከተራራ አናት ላይ ከሚገኝ ሜዳማ ቦታ ላይ ጨንቻ ከተማ ነው የተወለደው:: ከጋሞ ሰንሰለት ተራራዎች አንዱ ጫፍ ላይ የሚገኝ ጠረጴዛ ነው ይላታል፤ጨንቻን ሲገልጣት፡፡  ከ 2ኛ- 6 ኛ ክፍል እዚያው ጨንቻ የተማረ ሲሆን የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በአዲስ አበባ ኮከበ ጽባህ እስከ ፲ኛ ክፍል ተምሮ አቋረጠ። ሆኖም በራሱ መንገድ ህግ ተምሮ መመረቅ ብቻ ሳይሆን በአለም አቀፍ ውድድሮችም ሁለቴ ተካፍሎ፣ከንጉሱ እጅም የወርቅ ኦሜጋ ሰአት ለመሸለም በቅቷል፡፡
በመጽሐፉ ውስጥ በወህኒ ቤት ሳሉ፣ በሙሉጌታ በቀለ አካሚነት (ገጽ15-18) ሰለሞን ደርቤን በእግሩ ማቆም መቻልን አልፎም ፈጣን ሆኖ የእስረኛ ምግብና ቡና አመላላሽ ተደርጎ መመደቡን አሳይቶ አስደምሞኛል:: የአገራችንን የአብያተ ክርስቲያኑንም ጭምር ድንቅ ውበት በማስቃኘት፣ ለቱሪዝም አዳዲስ አካባቢዎችን ለማስተዋወቅ ሞክሯል፡፡
በመጽሐፉ ላይ በጠቀሳቸው (ገጽ 25-34) በረዘነና በወይናይ ባለው ችግር መነሻነት በትግራይና በኤርትራ መካከል የነበረው ቅራኔ ምን እንደሚመስል እንድናይ ያደረገበት ዘዴ አስገርሞኛል:: የሕግ አዋቂነቱን ለአቀራረቡ ማነጻጸሪያ ተጠቅሞበታል፡፡ “ረዘነ ወልዱና ወይናይ ሁለት የተለያየ ባህርይ ያላቸው ሰዎች ናቸው። ረዘነ ተጫዋች፤ተግባቢ፣ደግ፤ገራገር፤ተናጋሪና በመጠኑም ቢሆን ችኩልም ነው። ፈጣን ነው ማለት ይቻላል። ሀብታም ነው ማለትም ይቻላል። ወይናይ ምስኪን ነው። ሁለመናው ምስኪን ነው። ከ3 አመት በላይ ሲኖር ከመንሾካሸክ ያለፈ ድምጽ ሲወጣው አልሰማሁም። -----” ይለናል።
በመጽሐፉ (ገጽ19-24) ጎንደሬውን፤ቀናና የዋሁን፤እንደወጣ የቀረውን ዶ/ር ካሳሁን መከተን ያነሳዋል፡- ‹‹ በቀን ቢያንስ አንዴ ሳያነሳቸው የማይውላቸው ሁለት ነገሮች አሉ። አንደኛው ስለደባርቅ/ዳባት ነው። የኢትዮጵያን ኋላ ቀርነት ማስረጃ ያደርጋቸዋል። እስከ ዛሬ ማብራት እንኳን አልገባላቸውም! ይላል። “ሶሻሊዝም፤ሶሻሊዝም!” ይላሉ ደባርቅ መብራት መች ገባ ?” ይላል። ይህችው ነች! አይለዋውጥም!”
ብዙ ባለታሪኮና ተረቶች መጽሐፉን አጣፍጦለታል፡፡  እናቱን አክብረው “እንዬ” እያሉ ባደጉት ጓደኞቹ በእነ ዶክተር ገዛኸኝ በላይና በፍስሀ ዘለቀ ታሪክ ውሰጥ አጥልቆ የመንፈስን ከመንፈስ ጋር መዋሃድ እንዲሁም የህዝብን ሥነልቦናዊ አመለካከትን እንድናይ ያደርገናል::
“ነፍጠኛ” ማለት አማራ ብቻ ነው ማለት እምነት እንጂ እውነት እንዳልሆነና “ነፍጠኛ” (117-151) በሚል የሚበጠብጠንን ጥያቄ ለመመለስ ናችሁ የተባልነውን ሳይሆን ውስጣችን ገብተን ሆነን ያለነውን እንድናስተውል ይጎተጉተናል፡፡ ጋሽ አሰፋ፤“አቅብጦኝ ከደርግ ጋር ገጠምኩ” ብሎ አያውቅም:: አምኖ እንጂ ምናምን ፍለጋ ወይም ሰው ገፍቶት እንዳልገባ በግልጽ አስቀምጦልናል:: እንዲያውም “በመሸ በጠባ ቁጥር በጥሼ የምቀጥለው ማተብ የለኝም !” ይለናል::
በትረካዎቹ ጸሃፊው በንባብ የዳበረና የበሰለ መሆኑን ከማሳየቱም ሌላ ወደ አሜሪካ ስለ መምጣትና መኖር ያካፈለው ምክርም በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡ ስለ ስደቱ ዓለም ችግርና ውጥንቅጥ ሲጽፍም፤ ስደተኛው በሃብት ድህነትና በአእምሮ  ድህነት መካከል ያለው ልዩነት የጠፋበት መምሰሉን ፍንትው አድርጎ ያሳየናል፡፡ በአጠቃላይ ጆሮ ጠገብነት ማወቅን አለመተካቱን ይገልጽልናል፡፡   
ጀግና ፍለጋ ጦር ሜዳ መሪዎች አምባ፣ የፖለቲካ ሰዎች አምባ እንሄዳለን:: ጀግና ሲገኝ አገር ያውቀዋል፤ ፀሃይ ይሞቀዋል:: ያልታወቁ በየቤቱ የታጨቁ ተራ ሰው የሆኑ ጀግኖች አሉ በማለት፣ በዕለት ተዕለት ኑሮአችን ያልተሰጣቸውን በመፈጸም የበለጠ ጀግና ስላደረጋቸው የአማቾቹ የቤት ሠራተኛ ስለሆነችው ስለ ወሎየዋ ዘውዲቱ አስማረ “የኔይቱ ጀግና!” (63-67) በሚል ርዕስ ይተርክልናል፡፡  “ጋሞ” ይላል “ጋሞ ግብር ገበረ እንጂ ሥርዓቱን አልገበረም” በማለት ጥፋቱን ስህተቱን በማመን መቀበልና ባደባባይ ይቅርታ መጠየቅ የጋሞነት መገለጫና አብሮ የተወለደ የውስጥ ባህርይ መሆኑን በመተንተን፣ ለየት ስላለው የአገርና የህዝብ አስተዳደር ሥርዓት ሲያጫውተን፤ አንዳንዶቻችን በአገራችን ውስጥ ይህ መኖሩን ባለማወቃችን እንቆጫለን:: ወደ ዛሬያችን ለማምጣት በምኞት እንጋልባለን::
 ሌላው የጋሽ አሰፋ ትልቅነቱ፣ እንደ አንዳንዶቹ ፀሃፊዎች በራሱ አራት ነጥብ ዘግቶ እመኑልኝ ሳይለን፣ “ያየሁትና የኖርኩት እንጂ ያጠናሁት አይደለም” ማለቱ ነው:: በትዝታዎቹ ውስጥ እየሾለከ የሁላችንንም ትዝታ ይቆሰቁሰዋል፡፡ በተለይ በመጽሃፉ የጠቀሳትን፣ ይህንን ማዕከል ‹‹ጣይቱ›› ብዬ እንድሰይም ምክንያት የሆነችኝን Empress Taytu and Menilik the II of Ethiopia ደራሲ ክሪስ ፕራውቲን  (Chris Prouty 111-115)  እንደኔው አግኝቶ ስላደነቃትና ስላሞካሻት ይበልጥ ተደስቻለህ::
ዛሬ በአገራችን ስለተንሰራፋው ሥርዓትም በማዘን እየገለጸ ወደተሻለ እንድንጓዝ ይማፀነናል:: በእስራት ብዛት የህዝብ ነጻነት ታፍኖ የቀረበት ዘመንም አገርም አለመኖሩን በማስረገጥ፣ለ“የጋራ ቤታችን ” የሚፈለገውን መጠነኛ ጥገና በማካሄድ ፈንታ መናድ የመረጡትን ያወግዛቸዋል፡፡ አገራቸውን ባለማወቅ ወይም ለማወቅ ባለመፈለግ፣ ነቀዝ የበላው ቤት እንድትሆን ማድረጋቸውን በመውቀስም፣የምትፈለገዋን  ከስህተቷ ልምድ የቀሰመች አዲሲቷ ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን እንድንገነባ ይጣራል:: የትዝታ ፈለግ ራስ ወዳዶች እራሳቸውን እንዲጠይቁና እንዲፀየፉም ይገፋፋል፡፡ በተለይም ገጽ 244 “አልዘቅጥም መባል ያለበት ወደ ታች ወደ ምድር ቤት ምን ያህል ሲዘቅጡ ይሆን?›› ሲል በመጠየቅ ‹‹ከዚህ በላይ አልወርድም በቃኝ አይባልም! በቃኝ አታውርደኝ ተብሎስ አይፀለይም …” በማለት እነዚህን ወገኖች ይሸነቁጣቸዋል:: ከቁጣ ይልቅም ወደ ዳኝነት፣ ወደ ማመዛዘን እንድናደላ  ይጋብዘናል::
 አብርሃም ሊንከን እንዳለውና ጋሽ አሰፋም በመጽሃፉ ላይ እንደጠቀሰው፤ ‹‹ማንንም ያለ ቂም እንድንመለከት፣ሁሉንም በልግስና እንድናቅፍ፣በሃቅ ላይ እንድንጸና፣አምላክም ይህንን ሐቅ እንድናይ እንዲረዳን እንማጸን”:: ኢትዮጵያውያንንም የማይመጣን ነገር ከመጠበቅ ረጅምና ዝነኛ ታሪካችን ይገላግለን !
ጋሽ አሰፋም፤ “እመለስበታለሁ “ እያለ ያለፋቸውን ጉዳዮች፡- ስለ እስረኛው ቡና ማፍያ፣ ስለ ሁለንተናዊ የኑሮ ዘርፍ ማሟያ፣ ስለ ቀኝ አዝማች ታዬና ስለ ኮሎኔል መንግስቱ ኃ/ማርያም፣ ስለ አሜሪካ አገር ድመትና ውሻ ዘውድ መጫን፣ ወዘተ አሰባስቦ ሁለተኛ መጽሐፉን ለአንባቢያን እንዲያደርስ ያብቃው::
  “በትዝታ ፈለግ” ምክንያት እኔም እንደ ጋሽ አሰፋ ግርጫ ቤት መስራት አማረኝ:: እኔም ጨንቻን ወደ ታች የዞዞን ተራራ ማዶ ለማዶ ማየት አማረኝ:: ጨንቻን ለመሞት ሳይሆን ለመኖር መረጥኳት!! እዚያ ሰው አይሞትምና…በዝግታ መራቅ…ባልተስተዋለ መልኩ ማለፍ…አማረኝ!
   በድጋሚ እንኳን ደስ አለህ !!!

  ይህን የማያደርጉ መገናኛ ብዙኃን እርምጃ ይወሰድባቸዋል
        በካምቦዲያ የሚገኙ መገናኛ ብዙኃን የአገሪቱን ጠቅላይ ሚኒስትር በተመለከተ በሚሰሯቸው ዘገባዎች ላይ ተገቢውን ክብር መስጠት እንደሚገባቸውና ሙሉ ማዕረጋቸውን መጥቀስ እንዳለባቸው በአገሪቱ የመረጃ ሚኒስቴር ትዕዛዝ እንደተሰጣቸው ቢቢሲ ዘገበ፡፡ሚኒስቴሩ ለአገሪቱ የህትመትና የኤሌክትሮኒክስ መገናኛ ብዙኃን በሰጠው መግለጫ እንዳሳሰበው፣ ከመጪው ነሐሴ ወር ጀምሮ በሚሰሯቸው ዘገባዎች ላይ የጠቅላይ ሚኒስትሩን፣ የባለቤታቸውንና የተወሰኑ ባለስልጣናትን ከእነ ሙሉ ማዕረጋቸው መጥራት ይገባቸዋል፡፡መገናኛ ብዙኃኑ የአገሪቱን መሪ በተመለከተ በሚሰሯቸው ዘገባዎች ላይ፣ “ጌታ ጠቅላይ ሚኒስትርና የጠቅላይ ጦር አዛዥ ሁን ሴን” በማለት ከነ ሙሉ ማዕረጋቸው እንዲጠሯቸው ማሳሰቢያ እንደተሰጣቸው የጠቆመው ዘገባው፣ ሚኒስቴሩ ይህን በማያደርጉ መገናኛ ብዙኃን ላይ እርምጃ እንደሚወሰድ ቢናገርም እርምጃውን በተመለከተ የጠቀሰው ነገር እንደሌላ አመልክቷል፡፡

   16 ሚ. ድምጾችን አግኝቷል፤ ወደ አገሪቱ ፕሬዚዳንትነት ተጠግቷል ተብሏል
     ፊሊፒንሳዊው የአለም የከባድ ሚዛን ሻምፒዮን ማኒ ፓኪዮ ከትናንት በስቲያ ይፋ በተደረገው የአገሪቱ የላዕላይ ምክር ቤት አባላት ምርጫ ውጤት፣ ለምክር ቤት አባልነት የሚያበቃውን ድምጽ በማግኘት አሸናፊ መሆኑንና ወደ አገሪቱ ፕሬዚዳንትነት ተጠግቷል መባሉን ሮይተርስ ዘገበ፡፡ ባለፈው ሳምንት የአገሪቱ ምክር ቤቶች ምርጫ መከናወኑን ያስታወሰው ዘገባው፤የምርጫ ኮሚሽኑ ሃሙስ ዕለት ይፋ ባደረገው የምርጫ ውጤት፣ የአገሪቱ የላዕላይ ምክር ቤት አባል ለመሆን የሚያስችላቸውን ድምጽ ካገኙ አዳዲስ ተወዳዳሪዎች መካከል፣ ከ16 ሚሊዮን በላይ ድምጾችን ያገኘው ቦክሰኛው አንዱ መሆኑን አስታውቋል ብሏል፡፡
“በቦክሱ አለም ሳደርገው እንደቆየሁት ሁሉ፣ ወደ ፖለቲካው ስገባም፣ አገሬን ለመጥቀም በትኩረትና በስነ-ምግባር ተግቼ እሰራለሁ!... እንደ አንድ አዲስ የምክር ቤት አባልነቴ፣ በሁሉም ደረጃዎች ትምህርት በነጻ የሚሰጥበትን ሁኔታ ለመፍጠር የተቻለኝን ጥረት አደርጋለሁ” ብሏል የ37 አመቱ ቦክሰኛ ፓኪዮ፣ የምርጫ ውጤቱ ይፋ መደረጉን ተከትሎ ከጋዜጠኞች ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ፡፡
ፓኪዮ ባለፈው አመት በተከናወነውና የክፍለ ዘመኑ ፍልሚያ በተባለው የቦክስ ግጥሚያ ላይ ከታዋቂው ፍሎይድ ሜዌዘር ጋር ተጋጥሞ ድል ባይቀናውም ምርጫው ከመከናወኑ ከአንድ ወር በፊት ከአሜሪካዊው የከባድ ሚዛን ሻምፒዮን ቲሞቲ ብራድሊ ጋር በላስቬጋስ የቦክስ ግጥሚያ አድርጎ ድል እንደቀናውም ዘገባው አስታውሷል፡፡

    በዮናስ ሲሳይ ፕሮሞሽን የተዘጋጀውና “ሀገር፣ ባህል ማንነት” በሚል መሪ ቃል የሚቀርበው “ሄሎ ኢትዮጵያ”
የባህል ምሽት ሰኔ 20 ቀን 2008 ዓ.ም ሰኞ ምሽት በሀርመኒ ሆቴል ይካሄዳል፡፡ በዝግጅቱ ላይ በርካታ ባህላዊና ኪነጥበባዊ ድግሶች እንደሚቀርቡም አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡ በእለቱ በተለያዩ የውዝዋዜ ቡድኖች ባህላዊ ውዝዋዜ፣በሄሎ ኢትዮጵያ የባህል ሙዚቃ ቡድን የሚቀርብ የባህል ሙዚቃ ትርኢት እና የጋዜጠኛ ሰለሞን ታደሰ የተመረጡወጎች ለታዳሚ ይቀርባሉ የተባለ ሲሆን፤ የተለያዩ እውቅ የኪነ - ጥበብ ባለሙያዎች “ሀገር ማለት” በሚል መነሻ ሀሳብ ስለ አገራችን ባህልና ወግ ሀሳቦችን በማንሸራሸር ታዳሚውን እያዝናኑ እንደሚያስተምሩ የሄሎ ኢትዮጵያዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ቴዎድሮስ ሲሳይ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡

     በረቡኒ፣ መባ፣ ከዕለታት፣ ጢባጢቤና በሌሎችም ፊልሞቿ አድናቆትን ያተረፈችው ደራሲና ዳይሬክተር
ቅድስት ይልማ ስራ የሆነውና “ሰላም ነው?” የሚል መጠሪያ የተሰጠው ፊልም ከነገ በስቲያ በብሔራዊ
ቴአትር አዳራሽ ከቀኑ 11፡00 ሰዓት ጀምሮ ይመረቃል፡፡ የ1፡25 ሰዓት ርዝማኔ ያለውና የፍቅር ኮሜዲ
ዘውግ ያለው ፊልሙ የሰውን እድሜና እድል የሰረቀ ሰው በምንና እንዴት ይቀጣል በሚለው ላይ
እንደሚያጠነጥን የፊልሙ ፕሮዲዩሰር ፀጋነሽ ሃይሉ እና የሌሊያና ፊልም ፕሮዳክሽን ዋና ሥራ አስኪያጅ
ተናግራለች፡፡ፊልሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ አንድ አመት የፈጀ ሲሆን በፊልሙ ላይ ፀጋነሽ ሃይሉ ኤርሚያስ
ታደሰ አስኒክ በቀለ፣ ቴዎድሮስ ወዳጄና ሌሎችም አንጋፋና ወጣት ተዋንያን ተሳትፈውበታል፡፡

ከዝነኛው ኤዞፕ ተረቶች አንዱ እንዲህ ይላል፡-
ከዕለታት አንድ ቀን ተኩላዎች ወደ ውሾች መንደር መጡ ይባላል፡፡
“እንደምናችሁ ውሾች?”
ውሾችም፤
“እኛ ደህና ከርመናል፡፡ እናንተስ ተኩላዎች እንዴት ሰነበታችሁ?” አሉ፡፡
ተኩላዎችም፤
“እናንተ ውሾች በጣም ታሳዝኑናላችሁ”
“ለምን?”
“እስከዛሬ እኛና እናንተ ጠላት መሆናችን እጅግ ያሳዝናል፡፡ አለመተሳሰባችንና              አለመነጋገራችን ነው እንጂ ተስማምተን መኖር እንችል ነበር”
ውሾችም፤
“ኑሯችን ለየቅል ሆኖ እንዴት አብረን መኖር እንችላለን” አሉ፡፡
ተኩሎችም፤
“ዋናው ችግር በእርግጥ እሱ ነው፡፡ በመልክና በሁኔታችን በጣም እንመሳሰላለን፡፡ አፋችን፣
ጆሯችን፣ እግራችን ጭራችን …ሁሉ ነገራችን ተመሳሳይ ነው፡፡
ዋናው ልዩነታችን የሥልጠና ጉዳይ ነው፡፡
1ኛ) የምንኖረው በነፃነት ነው
2ኛ) እናንተ የሰው ልጅ ባሪያ ናችሁ፡፡ የሰው ልጅ እንደፈለገ ይቀጠቅጣችኋል፡፡
3ኛ) አንገታችሁ ላይ ሠንሠለት አስሮ ሣጥን ውስጥ ከቶ ያሳድራችኋል፡፡
4) የከብት መንጋ ያስጠብቃችኋል፡፡ ያለፍላጐታችሁ የሰው ከብት ስታዩ ትውላላችሁ፡፡
5ኛ) ለዚህ ሁሉ ልፋታችሁ የተጋጠ አጥንት ነው የሚወረውርላችሁ፡፡
ስለዚህ ከዚህ መከራ መገላገል አለባችሁ፡፡ ቢበቃችሁ ይሻላል፡፡” አሏቸው፡፡
ውሾችም፤
“የተናገራችሁት ዕውነት ነው፡፡ ነገር ግን ምን ማድረግ እንዳለብን አናውቅም” አሉ፡፡
ተኩላዎችም፤
“እኛ የመጣነው ዘዴውን ልንነግራችሁ ነው” አሉ፡፡
ውሻዎች በጥድፊያ፤
“ምንድነው ዘዴው?” አሉና ጠየቁ፡፡
ተኩላዎችም፤
“ዘዴውማ ከብቶቹን ለእኛ ስጡንና ወደ እኛ ጫካ ይዘናቸው ሄደን፣ የሰቡ የሰቡትን እየበላን፣
መጨፈርና መዝናናት ነው፡፡
እዚህ የሰው ልጅ ባሪያ ከመሆን ይሄ የነገርናችሁ ዘዴ አይሻልም?” አሏቸው፡፡  
ውሾች፤
“ሀሳቡን በደስታ እንቀበላለን፡፡ ድንቅ ሃሳብ ነው፡፡ ከብቶቹን እየነዳን አብረን እንሂድና
እንደሰት፡፡ ነፃ እንውጣ” አሉ፡፡ ተኩላዎችና ውሻዎች ተያይዘው፣ ከብቶቹን እየነዱ ወደ ዱር
ሄዱ፡፡
ተኩላዎቹ ግዛታቸው መድረሳቸውን ካረጋገጡ በኋላ ግን፤ ውሻዎቹን አንድም ሳያስቀሩ
ቦጫጭቀው ጨረሷቸው፡፡
***
“የባሰ አለ አገርክን አትልቀቅ” ይላል አበሻ ሲተርት፡፡ “ጠላ አገኛለሁ ብለህ፣ ውሃ ረግጠህ አትሂድ”ም ይላል፡፡ ያ ማለት ግን የታሠርክበትን ሠንሠለት ለመበጠስ አትሞክር፤ ዘላለም በባርነት ኑር ማለት አይደለም፡፡ ከበጠስክ በኋላ የት እንደምትደርስ በትክክል ዕወቅ፤ ቀጥለህም “ከዚያ በኋላስ?” ብለህ ጠይቅ ነው፡፡ አንድ ጥቁር አሜሪካዊ የትምህርት ሰው (academician) ስለ አፍሪካውያንና ስለ ነጮች ልዩነት ሲናገር፤ “አፍሪካውያን (ጥቁሮች) እጅግ ታታሪ ናቸው፡፡ ግባቸውንም ይመታሉ፡፡ ችግሩ የሚመጣው ከዚያ ቀጥሎ ነው፡፡ ይኸውም አንድ ግብ ሲመቱ “ቀጥሎ ምን መደረግ አለበት?” አይሉም፡፡ ነጮቹ ያንን መነሻ አድርገው ገና ወደ ላይ ይስፈነጠራሉ፡፡ አይ ፈረንጅ! ፈረንጅ የነካው ነገር እኮ ተዓምር ነው የሚፈጥረው” እንላለን፤ አለ፡፡ ይህንን በአበሽኛ ማሰብ ነው የሚጠበቅብን፡፡ ከሁሉም ያገኘነውና የተረፈን የስብሰባ ባህል ነው፡፡ ደራሲ በዓሉ ግርማ፤ “ህይወት ራሷ የተራዘመ ስብሰባ መሰለችኝ” እንዳለው ነው፡፡ ዛሬ ያውም ብሶ ተባብሶ ነው!! ሁኔታዎችን ተቆጣጣሪ ጠፋ፡፡ የትራፊክ አደጋ አንዱ ምሳሌ ነው፡፡ “ለመንገደኛ ቅድሚያ ባለመስጠት የተከሰተ ነው!” እየተባለ፤ “የሞኝ ለቅሶ መልሶ መልሶ” ሆነናል፡፡ ቢያንስ የዓለም ባንክ ሪፖርት የጠቀሰውን “የኢትዮጵያ የትራፊክ አደጋ ችግር፤ ትንሽ ያለማገናዘብ (Lack of commonsense) ችግር ነው” ያለውን ልብ ማለት ያባት ነው፡፡
 የኢኮኖሚ ችግራችንም ቢሆን እጅግ ቅጥ ያጣ ነው፡፡ የኢኮኖሚ ባለሙያዎቻችንም ነገር “ቄሱም ዝም ዳዊቱም ዝም” ነው! የስኳር ኮርፖሬሽን መቀመቅ መግባት አሰቃቂ ነው፡፡ ወይ በሰዓቱ ለህዝብ አልተነገረ፣ ወይ አስቀድሞ አደጋው በባለሙያዎቻችን አልተተነበየ፤ “አይመጣምን ትተሽ ይመጣልን ጨምሪበት” የሚለውን እንኳ ተረት አለማሰብ ከተማረ የማይጠበቅ ነው፡፡ ያን ካላሰብን፤ ቢያንስ “የተማረ ይግደለኝ!” ለማለት እንኳ አቅም ማጣታችን ነው! “የተማረ ይግደለኝ የምትል ከሆነ፤ ዩኒቨርሲቲ ደጃፍ ሄደህ ተንከባለል” የሚለውን ተረባዊ አባባል ተቀበል፤ የሚለውን ተግባራዊ ማድረግ ነው፡፡ ችግሩ ትምህርቱ ምሁር ሊፈጥር ባለመቻሉ ለሁሉም የዕቃ-ዕቃ ጨዋታ መሆኑ ነው! ጣጣችን ብዛቱ ይዘገንናል፡፡ መንገዶች ተሰሩ እንጂ ጠጋኝ የላቸውም! ኮንዶሚኒየሞች ከተሰሩ እና ከተሸጡ በኋላ ተከታታይ የላቸውም! ገበያዎች የሸማቹ ኪስ እስካለ ድረስ እንደፍጥርጥራቸው የሚባሉ ከሆኑ ውለው አድረዋል፡፡ አንድ የውጪ አገር ዜጋ እንደታዘበው፤ “የቢሮ ሰራተኞች እርስ በርስ ተቆላልፈዋል፡፡ በዚያው ሥራውም አብሮ ተቆልፏል” ብሎናል! የሀገራችንን ሁልቆ መሳፍርት የሌላቸው ችግሮች ለመፍታት የሚመሳሰሉ ሰዎች አንድ ላይ መሆናቸው ወሳኝ ነው! አፍና ልብ መገናኘታቸውም ዋና ነገር ነው፡፡ ዘይትና ውሃ ሆኖ ሥራ መስራት፣ ልማት ማልማት ብሎ ነገር እንዲያው ጨዋታ ነው! “ወመቴን ከአለሌ፣ ጨውን ከአሞሌ” መለየት ግድ ነው!” ከምትጣላው ጋር ገበታ ከመቅረብ፣ ከምትወደው ጋር መንገድ ጀምር! የሚባለው ለዚህ ነው!!