Administrator

Administrator

 የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር “የሂስ ጥበብ ሂደት በኢትዮጵያ” በሚል ርዕስ የተዘጋጀ ጥናታዊ ፅሁፍ ዛሬ
ከረፋዱ 3፡00 ጀምሮ በወመዘክር አዳራሽ ያቀርባል፡፡
   በጥናቱ ላይ በርካታ የስነ ፅሁፍ ባለሙያዎች፣ ደራሲያንና አንባብያን ተገኝተው ውይይት እንደሚደረግበት ተጠቁሟል፡፡ በውይይቱ ፍላጎት ያለው ሁሉ እንዲገኝና ሀሳብ እንዲያዋጣ ደራሲያን ማህበር ጥሪ አቅርቧል፡፡

  በአማረች ጎሹ የተዘጋጀው “ገዥነት” የተሰኘ አዲስ መፅሀፍ ገበያ ላይ ዋለ፡፡ መፅሀፉ በዋናነት ፍልስፍናዊ፣
ስነ- ልቦናዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ ያጠነጥናል ተብሏል፡፡ በ110 ገፆች የተቀነበበው መፅሐፉ፤ በ40 ብር
ለገበያ መቅረቡም ታውቋል፡፡

አብርሃም ግዛው ኢንተርቴይመንትና ስራዎች ድርጅት ከካሌብ ሆቴል ጋር በመተባበር ‹‹ድሮና ዘንድሮ›› የተሰኘ ዓለም አቀፍ የፍቅረኞች ቀንን ታሳቢ ያደረገ የመዝናኛ ፕሮግራም ማክሰኞ ይካሄዳል፡፡
    በፕሮግራሙ ላይ ታዋቂ ሰዎች፣ ረጅም ጊዜ በትዳር ያሳለፉ ጥንዶች የፍቅር ህይወታቸውን የሚያወጉበትና ልምድ የሚያካፍሉበት መድረክ መዘጋጀቱ የተገለፀ ሲሆን “የፍቅረኞች ቀን” በአገራችን መከበሩ ጥሩና መጥፎ ጎኑ ተነስቶ ውይይት ይደረጋል ተብሏል፡፡ በተጨማሪ አዝናኝ ገጠመኞች፣ ሙዚቃ፣ ትዊስትና ሳልሳ ዳንስ፣ ስታንዳፕ ኮሜዲና ሌሎችም የመዝናኛ ፕሮግራሞች ለታዳሚው እንደሚቀርቡ ለማወቅ ተችሏል።

ከአሜሪካ ታላላቅ ኩባንያዎች ግማሽ ያህሉ በስደተኞች የተቋቋሙ ናቸው

     ጎግል፣ አፕል እና ማይክሮሶፍትን ጨምሮ 127 የአሜሪካ ታላላቅ ኩባንያዎች፣ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በቅርቡ ያወጡት የስደተኞች የጉዞ ገደብ የስደተኞችን ህጎችና ህገ-መንግስቱን የሚጥስ ነው በሚል የተቃወሙት ሲሆን በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ በጋራ ክስ መመስረታቸው ተዘግቧል፡፡
በአብዛኛው በቴክኖሎጂ መስክ ላይ የተሰማሩት እነዚህ ኩባንያዎች፣ በጋራ በመሰረቱት ክስ፤ ስደተኞች በአሜሪካ ኢኮኖሚ ላይ ቁልፍ ሚና እንደሚጫወቱ በመጠቆም፣ ትራምፕ ስደተኞች ለተወሰነ ጊዜ ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ መከልከላቸው በአገሪቱ ኩባንያዎች ላይ ከፍተኛ ጉዳት የሚያደርስ በመሆኑ ሊነሳ ይገባል በሚል በክሳቸው ማመልከታቸውን ሲኤንኤን ዘግቧል፡፡ ስደተኞች ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ መከልከላቸው የአገሪቱ ኩባንያዎች የውጭ አገራት ምርጥ ባለሙያዎችን እንዳይቀጥሩና እንዳያሰሩ እክል ይፈጥራል ያሉት ኩባንያዎቹ፤ ተመልሰው የመግባታቸው ጉዳይ አስተማማኝ ካለመሆኑ ጋር በተያያዘ ሰራተኞቻቸውን ወደ ሌሎች አገራት ለስብሰባና ለልምድ ልውውጥ ለመላክ እንደሚያስቸግራቸውም ገልጸዋል፡፡
ከአሜሪካ 500 ታላላቅ ኩባንያዎች መካከል 200 ያህሉ በሌሎች አገራት ስደተኞችና ከስደተኞች በተወለዱ ልጆች የተቋቋሙ መሆናቸውን ታዋቂው ፎርቹን መጽሄት በቅርቡ ይፋ ባደረገው መረጃ ማስታወቁን ያስታወሱት ኩባንያዎቹ፤” ይህም በንግድና ቢዝነሱ መስክ የጎላ ሚና የሚጫወቱትን ስደተኞች ወደ አገሪቱ እንዳይገቡ መከልከል ኢኮኖሚውን ማዳከምና አዳዲስ ኩባንያዎች እንዳይፈጠሩ እንቅፋት መፍጠር እንደሆነ ያመለክታል” ማለታቸውንም ዋሽንግተን ፖስት ዘግቧል፡፡

በፕሬዚዳንትነት ደመወዝ ካገኙት በደራሲነት ያገኙት በ5 እጥፍ ይበልጣል
     የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፤ ከሴኔት አባልነት እስከ ፕሬዚዳንትነት በፖለቲካው አለም በነበራቸው የ12 አመታት ቆይታ፣ የሚስታቸውን ገቢና ከመጽሃፍት ሽያጭ ያገኙትን ገንዘብ ጨምሮ በድምሩ 20.5 ሚ. ዶላር ማግኘታቸውን ፎርብስ መጽሄት በሳምንቱ መጀመሪያ ባወጣው ዘገባ ገልጧል፡፡
ኦባማ እና ባለቤታቸው ሚሼል እ.ኤ.አ ከ2005 እስከ 2016 ባሉት አመታት፣ ከኩባንያ ቦርድ አባልነት 130 ሺህ ዶላር፣ ከፕሬዚዳንትነት ደመወዝ 3.1 ሚሊዮን ዶላር፣ ከሴኔት አባልነት ደመወዝ 610 ሺህ ዶላር፣ ከሚስታቸው የቺካጎ ዩኒቨርሲቲ ደመወዝ 760 ሺህ ዶላር፣ ከመጽሃፍት ሽያጭ 15.6 ሚሊዮን ዶላር እንዲሁም ከተለያዩ ገቢዎች 250 ሺህ ዶላር - በድምሩ 20.5 ሚሊዮን ዶላር ገቢ አግኝተዋል ተብሏል፡፡
ኦባማ በ12 አመታት ካፈሩት አጠቃላይ ገንዘብ ከሰባ በመቶ በላይ የሚሆነውን ያገኙት ለንባብ ካበቋቸው መጽሃፍት ሽያጭ ሲሆን፣ ኦዳሲቲ ኦፍ ሆፕ እና ኦፍ ዚ አይ ሲንግ - ኤ ሌተር ቱ ማይ ዶውተርስ ከተሰኙት ሁለት መጽሃፍት ብቻ 8.8 ሚሊዮን ዶላር ማግኘታቸው ተነግሯል፡፡
ኦባማ በፕሬዚዳንተነት ስልጣን ላይ በቆዩባቸው ስምንት አመታት ብቻ 10.8 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘታቸውን የጠቆመው ፎርብስ፤ ከዚህ ገንዘብ ውስጥ 3.1 ሚሊዮን ዶላር ያህሉ ከመንግስት በደመወዝ መልክ የተከፈላቸው፣ 120 ሺህ ዶላር የሚሆነው ደግሞ ከኢንቨስትመንቶች በትርፍ መልክ ያገኙት እንደሆነ ገልጧል፡፡
በ2009 አመት 5.6 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ያገኙት ኦባማ፣ በፕሬዚዳንትነት በቆዩባቸው አመታት ገቢያቸው ከአመት አመት እየቀነሰ በመምጣት በ2015 ላይ 450 ሺህ ዶላር መድረሱን ያስታወሰው ፎርብስ፤ ይህም የሆነው የመጽሃፍት ሽያጭ ገቢያቸው እያሽቆለቆለ በመምጣቱ ሰበብ ነው ብሏል፡፡
ፕሬዚዳንት ኦባማና ባለቤታቸው ሚሽል ኦባማ እ.ኤ.አ ከ2005 እስከ 2015 ድረስ ባሉት አስር አመታት ካገኙት አጠቃላይ ገቢ 8 በመቶ ያህሉን ወይም 1.6 ሚሊዮን የሚሆነውን ለበጎ ምግባር ስራ በስጦታ መልክ ማበርከታቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

ተመድ የአገሪቱን ባለስልጣናት በጦር ወንጀል እንዲከስ ተጠይቋል
     የሶርያ መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት በአራት አመታት ጊዜ ውስጥ ከ13 ሺህ በላይ ሰዎችን በጅምላ በስቅላት ማስገደላቸውን አለማቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች አምነስቲ ኢንተርናሽናል ባለፈው ማክሰኞ ባወጣው ሪፖርት አስታውቋል፡፡
ተቋሙ ባወጣው ሪፖርት እንዳለው፣ እ.ኤ.አ ከ2011 እስከ 2015 በነበሩት አመታት፣ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ባሻር አላሳድ ምክትሎችን ጨምሮ ከፍተኛ ባለስልጣናት ባስተላለፏቸው የግድያ ትዕዛዞች፣ ከአገሪቱ መዲና ደማስቆ በስተሰሜን በሚገኘው ሳይድኒያ የተባለ እስር ቤት ውስጥ ከ13 ሺህ በላይ ዜጎች በአሰቃቂ ሁኔታ በስቅላት ተገድለዋል፡፡
በእስር ቤቱ እጅግ ዘግናኝ የግርፋትና የማሰቃየት ተግባራት ይፈጸሙ እንደነበር ያወሳው ተቋሙ፤ በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ በእስር ቤቱ በየሳምንቱ በአማካይ እስከ 50 የሚደርሱ ሰዎች በስቅላት ይገደሉ እንደነበር በመጥቀስ፣ ከ2015 በኋላ ባለው ጊዜ ውስጥም በሺህዎች የሚቆጠሩ ሌሎች ሰዎች በተመሳሳይ ሁኔታ ተገድለዋል ብሎ እንደሚያምን አስታውቋል፡፡
በእስር ቤቱ ታስረው የነበሩ 31 እስረኞችን፣ ከ50 በላይ ባለስልጣናትንና ባለሙያዎችን በማነጋገር ያገኘውን መረጃ መሰረት አድርጎ ሪፖርቱን ማጠናቀሩን የጠቆመው ተቋሙ፤ አብዛኛዎቹ ግድያዎች የተፈጸሙት ከ2 ደቂቃ በላይ በማይዘልቁ የይስሙላ የፍርድ ቤት ክርክሮች በተላለፉ ውሳኔዎች ይሁን እንጂ፣ የግድያዎቹ ትክክለኛ መነሻ በከፍተኛ ባለስልጣናቱ የተላለፉ ፖለቲካዊ ውሳኔዎች ናቸው ብሏል፡፡
የሶርያ መንግስት ባለስልጣናት በእስር ቤቱ የፈጸሙት የስቅላት ግድያ ድርጊት በጦር ወንጀለኝነት ያስከስሳቸዋል ያለው ተቋሙ፤ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በጉዳዩ ዙሪያ ተጨማሪ ምርመራ እንዲያደርግና ባለስልጣናቱን ለህግ እንዲያቀርብ ጠይቋል፡፡

 የሩስያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፤ የአገሪቱ ጦር ወረራ ቢፈጸምበት በአስተማማኝ ሁኔታ መመከት የሚችልበት ወቅታዊ ዝግጁነት እንዳለው የሚያረጋግጥ፣ አፋጣኝ ፍተሻ እንዲደረግና አየር ሃይሉ ለጦርነት ብቁ በሆነ መልኩ እንዲዘጋጅ ድንገተኛ ትዕዛዝ ማስተላለፋቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
የአገሪቱን የመከላከያ ሚኒስትር ሰርጌ ሾይጉን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ፕሬዚዳንት ፑቲን የአገሪቱ የመከላከያ ተቋማትና ወታደሮች ለጦርነት ዝግጁ መሆናቸውን ለመገምገም የሚያስችል ምርመራ እንዲደረግ ባለፈው ማክሰኞ ያዘዙ ሲሆን፣ የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናትም ጦሩን ዝግጁ የማድረግ ስራ መጀመሩን አረጋግጠዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ይህንን ትዕዛዝ ያስተላለፉት ሩስያ ከአንዳንድ የኔቶ አባል አገራትና ከሌሎች የአለማችን ሃያላን አገራት ጋር ያላት ግንኙነት ውጥረቱ እየጨመረ ባለበት ወቅት ነው ያለው ዘገባው፤ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕም በቅርቡ የሩስያን ወታደራዊ ዘመቻዎች መኮነናቸውን አስታውሷል፡፡
ሩስያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ወታደራዊ እንቅስቃሴዋንና ዝግጁነቷን እያስፋፋች መምጣቷንና በአዲሱ የፈረንጆች አመት 2017፣ የጦር ታንኮችን ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደግን ጨምሮ ወታደራዊ አቅሟን ይበልጥ ለማጠናከርና ለማስፋፋት አቅዳ እየሰራች እንደምትገኝም ዘገባው ጠቁሟል፡፡

ወደዚህ ዓለም የመጣችው በኃይል ጥቃት ነው። እናቷን አንድ ሻምበል አስገድዶ ይደፍራታል። በዚያው ጥቃት ተፀነሰች፡፡ እንደማንኛውም ህፃን ከ9 ወር በኋላ በደብረማርቆስ ከተማ ተወለደች። እንደ ወጉ ቢሆን ህፃን ልጅን እናትና አባት ነበሩ የሚያሳድጉት፡፡ እሷ ግን ለዚህ ፀጋ አልታደለችም። አባቷን ስለማታውቅ እናቷ ብቻዋን አሳደገቻት - መንበረ አክሊሉን፡፡
አሜሪካ ሳንፍራንሲስኮ ነዋሪ የሆነችውን ወ/ሮ መንበረን አግኝቼ ይህንን ቃለ ምልልስ ያደረግነው፣ ባለፈው ሳምንት በኢትዮጵያ የሊንከን ኮሌጅ ለ6ኛ ዙር ኤምቢኤ፣ ለመጀመሪያ ጊዜ በቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን ያስተማራቸውን 45 ተማሪዎች በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን አዳራሽ ባስመረቀበት ወቅት የቢዝነስ ተሞክሮዋን፣ ያሳለፈችውን መጥፎ ህይወትና አሁን የደረሰችበትን ስኬት ለተማሪዎቹ እንድትናገር ዩኒቨርሲቲው ጋብዟት መጥታ ነው፡፡
እናቷ ብቸኛ በመሆንዋ የራሷንና የልጇን ህይወት ለመለወጥ ትፍጨረጨር ነበር፡፡ ኑሮዋን ለማሸነፍ ጠጅ ንግድ ጀመረች፡፡ የጠጅ ንግዱ ደራላት፡፡ “የማገኘው ገንዘብ ለልጄና ለራሴ ኑሮ ይበቃናል፡፡ ተመስገን! ይህንኑ ይባርክልኝ” ብላ አልተቀመጠችም፡፡ እንዲያውም ኮማሪትነትን አጧጧፈችው፡፡
ጥረቷ ሰመረላትና ጠጅ ቤቱን ወደ ሆቴልነት ለወጠችው፡፡ ሆቴሉን ከፍታ ያለ ዕረፍት ስትሰራ ገበያው ደራላት፡፡ ደንበኞቿን ለማስደሰት ሌት ተቀን ስትጥር አንድ ቀን ያልታሰበ ነገር ተፈጠረ፡፡ በመጠጥ ቤቱ ሲጠጣ የቆየ አንድ ሻምበል ሰክሮ፤ “ሂሳብ አልከፍልም” በማለት አምባጓሮ ፈጠረ። በዚህ ጊዜ “የተጠቀምከውን ሂሳብማ ልትከፍለኝ ይገባል” በማለት ፖሊስ ስትጠራ፣ የታጠቀውን ሽጉጥ አውጥቶ ተኩሶ ገደላት፡፡
መንበረ በዚያን ወቅት የ10 ዓመት ልጅ ስትሆን፤ በንጉሥ ተክለሃይማኖት ት/ቤት የ6ኛ ክፍል ተማሪ ነበረች፡፡ እናቷ ስትገደል አይታለች፡፡ አሁን ወላጅ አልባ ሆነች፡፡ በዚህ ጊዜ አዲስ አበባ የነበሩት ታላቅ ወንድሟና ታላቅ እህቷ እናሳድጋታለን ብለው አመጧት፡፡ ዳግማዊ ምኒልክ 2ኛ ደረጃ ት/ቤት ገብታ ትምህርቷን እስከ 12ኛ ክፍል ተማረች፡፡
ታላቅ ወንድሟ “ዩኒቨርሲቲ ገብተሽ ትምህርትሽን ቀጥይ” ብሏት ነበር፡፡ እሷ ግን “ተዋናይ መሆን ነው የምፈልገው” ብላ አሻፈረኝ አለች፡፡ እንደፈለገችው የትወና ትምህርቱን ተከታትላ ተዋናይ ሆነችና ብሔራዊ ቴአትርና ራስ ቴአትር ተቀጥራ ሰራች፡፡
በዚህ ወቅት አለቃዋና የልጇ አባት ከሆነው ሰው ጋር ተዋውቃና ተግባብተው ፍቅር ጀመሩ፡፡ ፍቅረኛዋ ስኮላርሺፕ አግኝቶ ጣሊያን ከሄደ በኋላ፣ “ታዋቂ ተዋናይ መሆን ትችያለሽና እዚህ ነይ” ብሎ የግብዣ ወረቀት ላከላት፡፡ እሺ! ብላው ጣሊያን ሄደች፡፡ ቤተሰቦቿ (እህትና ወንድሟ) ወደ ጣሊያ መሄዷን አልወደዱም ነበር፡፡ ምክንያቱም እዚህም እያሉ ፍቅረኛዋ ጥሩ ሰው እንዳልሆነ ያውቃሉ፡፡ ይጎዳትና ይደበድባት ነበር፡፡ እንዲያውም አንድ ጊዜ አፍንጫዋን ሰብሯት ሆስፒታል ሁሉ ገብታ ነበር። በዚህ የተነሳ ተከትላው እንድትሄድ ስላልፈለጉ “ይቅርብሽ” ብለዋት ነበር፡፡
መንበረ ግን የወንድምና የእህቷን ምክር አልተቀበለችም፡፡ ወጣትነት፣ ፍቅርና ከሀገር የመውጣት ፍላጎቱ ተደማምረው ተከትላው ኢጣሊያ ሄደች፡፡ ሮም ከተማ አብረው መኖር ጀመሩ፡፡ የፍቅረኛዋ ባህርይ ግን አልተለወጠም፤ እንዲያውም ባሰበት፡፡ ሮም በደረሰች ሦስተኛ ወሯ ፀነሰች፡፡ ፍቅረኛዋ ይደበድባትና ይጎዳት ነበር፡፡ መጨረሻ ላይ ፊቷንና ክንዷን በሲጋራ አቃጠላት፡፡ ዘጠኝ ወር ሲሞላትም ጉዳትና ድብደባው አልቀረላትም፡፡ እንዲያውም ሊገድላት ይፈልግ ጀመር፡፡ በዚህ ጊዜ ግፉ ስለበዛባት ከቤት ወጥታ ጠፋች፡፡
ለመውለድ 6 ቀን ነበር የቀራት፡፡ ገንዘብ የላት፣ ቋንቋ አታውቅ፣ የምትጠጋው ዘመድ የላት፤ … ወጥታ ቤተ ክርስቲያን በረንዳ ላይ ተቀመጠች። ቀኑ እየመሸ ሲሄድ መጠጊያ ስለሌላት እዚያው በረንዳ ላይ ለማደር ወሰነች፡፡ በዚህ ጊዜ አማርኛ የሚናገሩ አንድ ኢጣሊያዊ ቄስ፤ አይተዋት ጠጋ ብለው ምን እንደሆነች ጠየቋት፡፡ እሷም ታሪኳን ዘርዝራ አጫወተቻቸው፡፡ ቄሱም፤ “ልትወልጂ ድርስ ስለሆንሽ መንገድ ላይ ማደር የለብሽም፤ እኔ ቦታ አገኝልሻለሁ” ብለው ወደ ማዘር ቴሬሳ የሴቶች መጠለያ ወሰዷት፡፡
መጠለያው ውስጥ በአልኮል፤ በአደንዛዥ ዕፅ፣ በሴተኛ አዳሪነት፣ … ወንጀል የተከሰሱ ሴቶች ነበሩ፡፡ ራሷን ከእነሱ ጋር አመሳስላ ቆየች፡፡ እዚያ በገባች በ6ኛ ቀኗ ልጇን ወለደች፡፡ ከ3 ወር በኋላ የቤት ውስጥ ሰራተኛነት ስራ አግኝታ ወጣች፡፡ ሳህን እያጠበች፣ ቤት እያፀዳች፣ ምግብ እየሰራች፣ ልብስ አጥባ እየተኮሰች፣ … አጠቃላይ የቤት ውስጥ ስራ እየሰራች ልጇን አሳደገች፡፡ ስራውን ወድዳና አክብራ፣ ልጇ 11 ዓመት እስኪሞላው ድረስ እዚያው ቤት ሰራች፡፡ በዚህ ጊዜ አንድ መጥፎ አጋጣሚ ተፈጠረ - አሰሪዋ ሞቱ፡፡
እሷም “እስከ መቼ ድረስ ነው በቤት ሰራተኝነት የምቀጥለው? ይኼ ስራማ የህይወቴ መጨረሻ መሆን የለበትም፤ ልጄ ነፍስ ካወቀልኝ ህይወቴን የመለወጥ ትልቅ ህልም አለኝ፡፡” በማለት አሰበች። ምን እንደምትሆን፣ ምን እንደሚያጋጥማት አታውቅም፡፡ ሆኖም “በምንም ዓይነት መንገድ እንደዚህ ሆኜ መቅረት የለብኝም፡፡ ጠንክሬ በሥነ - ሥርዓት ከሰራሁ፤ እለወጣለሁ” የሚል እምነትና ጥንካሬ በውስጧ ስለነበር፣ ሁለተኛ የስደት ህይወት ለመጀመር ልጇን ይዛ አሜሪካ ገባች፡፡
አሜሪካ ሳንፍራንሲስኮ ካሊፎርኒያ ውስጥ ሪችሞንድ በተባለች ከተማ አረፈች፡፡ እዚያም ሳሉቴ ኢቪታ (በጣሊያኒኛ ጤና ማለት ነው) በተባለ ሬስቶራንት ውስጥ በሰዓት ሰባት ዶላር እየተከፈላት፣ እንግዳ ሲመጣ ተቀብሎ ማስቀመጥ ሥራ አገኘች። በዚያን ጊዜ ለእሷ 7 ዶላር ትልቅ ገንዘብ ነበር። ሥራዋ፤ በፈገግታ እንግዶችን ተቀብሎ ወንበር ሰጥቶ ማስቀመጥ ቢሆንም፣ ስራው እንዳያመልጣት በማለት የማትሰራው ነገር አልነበረም፡፡ ግድግዳ ታጥባለች፣ መስኮት ትወለውላለች፣ ወለል ታፀዳለች። የሥራ ባልደረቦቿ “ይኼ ያንቺ ስራ አይደለም፡፡ ያንቺ ስራ ጥሩ ለብሶ፣ በር ላይ ቆሞ በፈገግታ ሰዎችን መቀበልና ማስቀመጥ ብቻ ነው” በማለት ይመክሯት ነበር፡፡ እሷ ግን ምክራቸውን አልተቀበለችውም፡፡ ኢጣሊያ እያለች ከንጋቱ 11 ሰዓት እስከ እኩለ ሌሊት ያለ ዕረፍት ትሰራ ስለነበር፣ አልከበዳትም፤ እንዲያውም አጠነከራት እንጂ፡፡ ደሞዟም 8፣ 9፣ 10፣ … ዶላር እያለ አድጎ የማታ ማታ የሬስቶራንቱ ሥራ አስኪያጅ ሆነች፡፡
በዚህ ዓይነት ለ6 ዓመት እንደሰራች ባለቤቱ ሳሉቴን መሸጥ ፈለገና ለሰራተኞቹ ማስጠንቀቂያ ሰጠ፡፡ በውሃ ላይ የተሰራ፣ ሳንፍራንሲስኮን ዙሪያዋን ማሳየት የሚችል በከተማዋ (ሪች ሞንድ) ትልቅ ሬስቶራንት ነበር ሳሉቴ፡፡ በሬስቶራንቱ ውስጥ መንበረ ተወዳጅ፡፡ ተወዳጅነትን ያገኘችው የኢጣሊያ ቋንቋ አቀላጥፋ ስለምትናገር፣ ጠንካራ ሰራተኛ ስለሆነች፣ የተዋናይነት ስሜትና ተግባቢነት በውስጧ ስላለ ነው፡፡ የእሷን ጥንካሬና ቅልጥፍና ለማየት የሚመጡ ደንበኞች “መንቢን ልናጣ ነው፣ ምን ይሻላል?” ይሉ እንደነበር ተናግራለች፡፡
ሳይደግስ አይጣላም እንዲሉ፣ ያላሰበችውና ያልጠበቀችው ነገር ተፈጠረ፡፡ “ስራ ፈልጉ” የሚል ማስጠንቀቂያ እንደተሰጣቸው፣ አንድ በስራዋና በቅልጥፍናዋ እንዲሁም በቋንቋዋ ይማረክ የነበረ ኢጣሊያናዊ ደንበኛቸው፣ “መንቢ፣ ምንድነው እቅድሽ?” ሲል ጠየቃት፡፡ እሷም፤ “ምንም! እቅድ የለኝም፡፡ ስራ እፈልጋለሁ፣ ወይም ሬስቶራንቱን የሚዙ ሰዎች ከቀጠሩኝ እዚሁ እሰራለሁ” አለች። ያ ኢጣሊያናዊ በማግሥቱ ከልጁና ከሚስቱ ጋር መጥቶ፣ “መንቢ፣ እኔም እንዳንቺ ከጣሊያ አገር በ13 ዓመቴ ወጥቼ ነው እዚህ ሀብታም የሆንኩት። ዓለም ለእኔ ጥሩ ስለሆነች ያገኘሁትን ሁሉ መልሼ ለሌሎች ሰዎች መስጠት አለብኝ” አላት፡፡ “እናስ?” በማለት ጠየቀችው፡፡ “እናማ፤ የትም አትሄጂም። ገንዘብ አበድርሻለሁ፡፡ ይህንን ሬስቶራንት ትገዣለሽ” አላት። መንበረም፣ “እኔ አልችልም። በምን እውቀቴ ነው የማስተዳድረው?” አለች፡፡ “ምንም እውቀት አያስፈልግሽም፡፡ ጠንካራ ሰራተኛ ነሽ፡፡ ለሬስቶራንቱ 24 ሰዓት ትሰሪ ነበር። ወደፊትም 24 ሰዓት መሥራት ነው፤ ለውጥ የለውም” በማለት ብትከስርም ምንም እንደማያገኝ እያወቀ     “በአምስት ዓመት ትከፍይኛለሽ፤ ካልቻልሽም ሌላ እጨምርልሻለሁ” በማለት አስፈርሞ ግማሽ ሚሊዮን ዶላር አበደራት።
መንበረ፣ ከልጅነቷ ጀምሮ ጠንካራ ሰራተኛ ስለሆነች፣ ብዙ ችግር ያሳለፈች፣ መኖሪያ አጥታ መጠለያ ውስጥ የኖረች ስለነበር … እኒህ ሁሉ መከራዎች ድፍረትና ጥንካሬ ሰጧት፡፡ ሌት ተቀን ጠንክራ በመስራት የአምስት ዓመቱን ብድር በአንድ ዓመት ከፍላ ጨረሰች፡፡ ይህን ዕዳ ለመክፈል ያየችው ፍዳ አይጣል ነው፡፡ ሌሊት መነሳት፣ ከወዲያ ወዲህ ሲወዛወዙ መዋል እጅግ ከባድ ነበር፡፡ ከመድከሟና ከመዛሏ የተነሳ መኪና መንዳት አቅቷት፣ ሦስትና አራት ቀን ሬስቶራንቱ ውስጥ ለማደር እንደተገደደች ትገልጻለች፡፡ “ዛሬ እኔም ሬስቶራንቱም ታዋቂ ሆነናል” ትላለች፤ መንበረ። በሳሉንቴ ሬስቶራንት 6 ዓመት በአስተናጋጅነት፣ 16 ዓመት በባለቤትነት በአጠቃላይ ለ22 ዓመታት መስራቷን፣ ሬስቶራንቱ 18 ሰራተኞች እንዳሉት ተናግራለች፡፡ መንበረ “እግዚአብሔር ለእኔ እንዲህ ደግ ከሆነ፣ እኔስ ምንድነው ማድረግ ያለብኝ” በማለት አሰበች፡፡ እዳዋን ከፍላ ከጨረሰች ከአንድ ዓመት በኋላ፤ “እኔም ከእነሱ አንዷ ነበርኩ” በማለት ጎዳና ተዳዳሪዎችን አሰበች፡፡ በዓመት አንድ ቀን “የድሆች ቀን” በማለት፣ 1,500 ለሚሆኑ የጎዳና ተዳዳሪዎች እራት ታበላለች፡፡ በሥነ ስርዓት ተቀብለው፣ ሁለትና ሶስት ሹካ አስቀምጠው፣ ክሪስታል ብርጭቆ አኑረው፣ እንደማንኛውም 100ና 200 ዶላር እንደሚከፍል እንግዳ ተስተናግደው ይሄዳሉ፡፡ ሐኪሞችን በማስተባበር ኢንፍሉዌንዛ እንዳይዛቸው ክትባት እንዲያገኙ፤ የደም ግፊት ካለባቸው እንዲለኩና ምክር እንዲሰጣቸው ይደረጋል፡፡ በራባቸው ጊዜ ደግሞ ወደ ሬስቶራንቱ መጥተው ምግብ እንዲወስዱ ነግረው ያሰናብቷቸዋል፡፡
ይህ በየዓመቱ የሚደረግ ግብዣ መንበረን በአሜሪካ እንድትታወቅ አደረጋትና “ሆሊ ኔምስ” የተባለ ዩኒቨርሲቲ፣ “ስደተኛ ሆና ይህን የመሰለ የተቀደሰ ተግባር በመፈጸሟ ልትሸለም ይገባል” በማለት የክብር ዶክትሬት ዲግሪ እንደሰጣት ገልጻለች፡፡ ከዚህም በተጨማሪ እሷን እያዩ ፈረንጆችም መተባበር ስለጀመሩ፣ በከተማዋ አስተዳደር የሚመራ ፋውንዴሽን ከፍታለች፡፡ ይህ ደግሞ ለሌላ ተግባር አነሳሳት፡፡
አሜሪካ ውስጥ “ማዘርስ ዴይ” ይከበራል። በዚህ ዕለት ባል ያላቸው ዕድለኛ እናቶች የሽቶ፣ የአበባ … ስጦታ ይበረከትላቸዋል፡፡ ጥሩ እራትም ይጋበዛሉ። መንበረ፤ በእናቶች ዕለት “በመጠለያ ውስጥ የሚኖሩ ድሃ እናቶችን እናስብ” በማለት በመጠለያ ውስጥ የሚኖሩትን እናቶች በሙሉ አሰባስባ እራት ታበላለች። ድሃ እናቶች ወደ ግብዣው ስፍራ ከመምጣታቸው በፊት ልጆቻቸውን የሚጠብቅላቸው ሰው ይመደብላቸዋል፣ ፀጉራቸውን እንዲሰሩ ይደረጋል፡፡ የአዕምሮ ሐኪሞችን አስተባብራ እንዲመረምሯቸው፣ እንዲመክሯቸውና እንዲያበረታቷቸው ታደርጋለች፡፡
የልጃገረዶች ፕሮጀክትም አላት፡፡ ጥሩ ውጤት ኖሯቸው ትምህርት ቤት መሄድ ለማይችሉ 8 ልጃገረዶች በየወሩ እየከፈለች በግል ት/ቤት እያስተማረች ነው፡፡ ይህ የልጃገረዶች ፕሮጀክት ወደ ኢትዮጵያም ዘልቋል፡፡ በደብረ ማርቆስ ከተማ ውስጥ የእናቷ ቤት በነበረበት ቦታ፣ ባለ 3 ፎቅ ህንፃ በ300 ሺህ ዶላር አሠርታ፣ 80 ልጃገረዶችን ለማስተማር ዝግጅት መጀመሯን ገልጻለች፤ ወ/ሮ መንበረ አክሊሉ፡፡
ያ በኢጣሊያ ማዘር ቴሬሳ መጠለያ ውስጥ የተወለደው የመንበረ ልጅ፤ በሚቀጥለው ዓመት ከኒውዮርክ ዩኒቨርሲቲ በዶክትሬት ዲግሪ ይመረቃል።     
ወ/ሮ መንበረ በዳንግላ ከተማ ጋሹና ሆቴል ውስጥ ሼፍ ሆና ስትሰራ፣ የቀድሞ ፍቅረኛዋ ፊቷ ላይ አሲድ ደፍቶባት ጉዳት ለደረሰባት መሰረት ንጉሤ 5 ሺህ ዶላር መላኳን፣ ሐኪሞች፣ የመሠረትን ጉዳት አይተው መታከምና መዳን እንደምትችል ስለገለጹላት አሜሪካ ወስዳ ለማሳከም ዝግጅት እያደረገች መሆኑን ተናግራለች፡፡   

6 ቢሊዮን ዶላር ያህል በሪልእስቴት ዘርፍ ኢንቨስት ተደርጓል ተብሏል

  አዲስ አበባ በሪልእስቴት ዘርፍ ኢንቨስትመንት ከአፍሪካ ከተሞች በ3ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝና የከተማዋ የሪልእስቴት ልማት ዘርፍ ኢንቨስትመንት፣ 6 ቢሊዮን ዶላር እንደሚደርስ የዓለም ባንክ ከትናንት በስቲያ ይፋ ባደረገው የአፍሪካ ዋና ዋና ከተሞች ወቅታዊ ሁኔታ አመላካች ሪፖርት አስታውቋል፡፡
የታንዛንያዋ ዳሬ ሰላም በሪልእስቴት ልማት ዘርፍ ከአፍሪካ ከተሞች በአንደኛ ደረጃ ላይ መቀመጧን የጠቆመው ሪፖርቱ፣ የከተማዋ የሪልእስቴት ኢንቨስትመንት 12 ቢሊዮን ዶላር እንደሚደርስ የገለጸ ሲሆን፣ የ9 ቢሊዮን ዶላር የሪልእስቴት ኢንቨስትመንት ባለቤት የሆነቺው የኬንያ ርዕሰ መዲና ናይሮቢ፣ በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝም አስረድቷል፡፡
በአፍሪካ ከተሞች የሪልእስቴት ዘርፍ ልማት እየተስፋፋ ቢመጣም፣ የከተማ ነዋሪዎች ከነፍስ ወከፍ ገቢያቸው ጋር ሲነጻጸር የመኖሪያ ቤት ፍላጎታቸውን ለማሟላት ከፍተኛ ገንዘብ እንደሚያወጡም የጠቆመው ሪፖርቱ፤ በአንዳንድ የአህጉሪቱ ከተሞች የመሬት ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ በመሄድ በአሜሪካ በሚሸጥበት ዋጋ መሸጥ መጀመሩንም አክሎ ገልጧል፡፡
የአህጉሪቱ የከተማ ነዋሪዎች ቁጥር እስከ 2050 ድረስ በ170 ሚሊዮን እንደሚጨምር እንዲሁም አሁን ያለው የከተማ ነዋሪ ህዝብ ቁጥር በ25 አመታት ጊዜ ውስጥ በእጥፍ በማደግ 1 ቢሊዮን ይደርሳል ተብሎ እንደሚገመት የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ይህም በመሆኑ የአህጉሪቱ ከተሞች የመኖሪያ ቤት ግንባታን ጨምሮ ከህዝብ ቁጥር እድገቱ ጋር የሚመጣጠን ሰፊ የመሰረተ ልማት አውታሮች ግንባታ ማካሄድ እንደሚጠበቅባቸው አስረድቷል፡፡
የአፍሪካ ከተሞች እጅግ ውድ ከሆኑ የአለማችን ከተሞች ተርታ እንደሚመደቡ የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ከሌሎች ተመሳሳይ ገቢ ያላቸው የአለማችን አገራት ከተሞች ጋር ሲነጻጸር በ30 በመቶ ያህል የበለጠ ውድ መሆናቸውንና ይህም ከተሞቹ አለማቀፍ ኢንቬስተሮችን እንዳይስቡ እክል እንደፈጠረባቸው ገልጧል፡፡

“ፐርሰንት ከደመወዝ ተቀንሶ አይከፈልም፤ አሠራሩም ሕጋዊ አይደለም” /ክፍለ ከተማው/
    በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፣ “የደብረ ተኣምራት ዳግማዊት ጻድቃኔ ማርያም ቤተ ክርስቲያን ካህናትና ሠራተኞች፤ ለተፈቀደላቸው የደመወዝ ጭማሪ ማጽደቂያ፣ ለሀገረ ስብከቱ ሓላፊዎች የተሰጠው ብር 50 ሺሕ ጉቦ እንዲመለስ ታዘዘ፤” በሚል ርእስ፣ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ባለፈው ሳምንት ያወጣው ዘገባ፣ “ያልተጣራና መሠረተ ቢስ ነው” ሲሉ ሀገረ ስብከቱና የደብሩ ጽ/ቤት አስተባበሉ፡፡
ቤተ ክርስቲያኗ ካላት ከማንኛውም ገቢ ላይ ሃያ በመቶውን የሀገረ ስብከቱን ድርሻ እንድትከፍል በቃለ ዐዋዲው መደንገጉን በማስተባበያቸው አስታውሰው፤ በዘገባው የተጠቀሰውና ከደብሩ ጽ/ቤት ወጣ የተባለው 50ሺ ብርም፣ በወቅቱ ያልተከፈለ የደብሩ የሃያ ፐርሰንት ውዝፍ ሒሳብ መሆኑን አስረድቷል፡፡ ይህም፣ ሀገረ ስብከቱን ወክሎ በሚሠራው በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ስም በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በተከፈተው ተንቀሳቃሽ ሒሳብ ገቢ መደረጉን በመጥቀስ ደረሰኙን በአስረጅነት አቅርቧል፡፡ “ወደ ተቋሙ ባንክ የገባውን ገንዘብ ለግለሰቦች እንደተሰጠ አስመስሎ መዘገቡ ሚዛናዊነት የጎደለው ነው፤” ሲልም ዘገባውን ተቃውሟል፡፡ የኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ፣ መጋቤ ሠናያት የቻለው ለማ በበኩላቸው፤ “የደብሩ የሃያ በመቶ ውዝፍ ዕዳ መከፈል ያለበት ከደብሩ ገቢ እንጂ ከሠራተኞች ደመወዝ ተቀንሶ መሆን የለበትም፤ የሁለት ወሩ የደመወዝ ጭማሪም የተቀነሰው፣ የጽ/ቤቱ ሓላፊዎች በራሳቸው ወስነው እንጂ፣ የሚመለከተው ሰበካ ጉባኤ በተገኘበት እንዳልሆነ ጽ/ቤታቸው ባደረገው የሰነድና የገጽ ለገጽ ማጣራት ማረጋገጡን ገልጸዋል፡፡ ገቢ ተደርጓል ስለተባለው 50ሺ ብር የተጠየቁት ሥራ አስኪያጁ፣ “የክፍለ ከተማው ጥያቄ የ50ሺሕ ብር አከፋፈል ሒደት አይደለም፤ ከግለሰቦች ላይ የተቀነሰው የገንዘብ አከፋፈል ሒደትና አሠራር ትክክል አይደለም፤ ፍትሐዊ አይደለም፤ ነው፤” በማለት ከደመወዝ ጭማሪው ጋር ግንኙነት እንደሌለው አስረድተዋል፡፡