Administrator

Administrator

የደራሲ አዳም ረታ ረዥም ልቦለድ “ሕማማትና በገና” ነገ ውይይት እንደሚካሄድበት ሚዩዚክ ሜይዴይ አስታወቀ፡፡ ውይይቱ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቤተመጻሕፍትና ቤተመዛግብት አዳራሽ ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ ለሦስት ሰዓታት ይዘልቃል፡፡ የመነሻ ሃሳብ በማቅረብ ውይይቱን ከሚዩዚክ ሜይዴይ ባለሙያዎች ጋር የሚመሩት የሥነጽሑፍ ባለሙያው አቶ ቴዎድሮስ አጥላው ናቸው፡፡

በኮሜዲያን ታሪኩ ሰማንያ እና ቢኒያም ዳና የተፃፈው “ሀ በሉ” ፊልም ነገ በሀዋሳ ከተማ ባህል አዳራሽ ይመረቃል፡፡ የ100 ደቂቃ ርዝመት ያለው አስቂኝ ፊልሙ፤ በአይዶል ውድድር ለመሳተፍ ከክፍለ ሀገር ወደ አዲስ አበባ በመጡ ሁለት ወጣቶች ላይ ያጠነጥናል፡፡
በፊልሙ ላይ ደራሲዎቹን ጨምሮ ካሙዙ ካሳ ማሚላ፣ ኪችሌ እና ሌሎችም ተውነዋል፡፡ በደቡብ ክልል የአማርኛ ለዛ የተሰራው ይሄ ፊልም፤ አዋሳን ጨምሮ በመላ ሀገሪቱ እንደሚታይ ማወቅ ተችሏል፡፡ ፊልሙ ሙሉ በሙሉ በሐዋሳ የተሰራ ሲሆን ፕሮዱዩሰሩ ቀደም ሲል “ቴክ ኢት ኢዚ” የተሰኘውን ፊልም ፕሮዱዩስ ያደረገው ሻና ፊልም ፕሮዳክሽን እንደሆነ ታውቋል፡፡

በአዲስ አድማስ “እንጨዋወት” አምዱ የሚታወቀው ደራሲና ወግ ፀሃፊ ኤፍሬም እንዳለ ያዘጋጀው “የዓለም ታላላቅ ታሪኮች ለሕጻናት” መፅሃፍ ለንባብ በቃ፡፡ መፅሃፉ የሮቢን ሁድ፣ ሮቢንሰን ክሩሶ፣ “ሪፕ ቫን ዊንክል እና ሌሎች ታላላቅ ሰዎችን ታሪኮች ይዟል፡፡ 86 ገፆች ያሉት የሕጻናት መጽሐፍ፤ በጃፋር መጻሕፍት መደብር በ20 ብር እየተሸጠ ነው፡፡ ኤፍሬም እንዳለ በቅርቡ ያሳተመውን የስኬት መፅሃፍ ጨምሮ የተለያዩ የወግና የትርጉም ሥራዎችን ለንባብ ማቅረቡ ይታወቃል፡፡

ማንኛውም ጤናማ ሰው ቢያንስ በሣምንት አንድ ቀን በፍልውሃ መታጠብ ይገባዋል

እርጅና የተጫጫናቸው ክፍሎች፣ የወላለቁ የቧንቧ መክፈቻና መዝጊያዎች፣ የተላላጡ ግድግዳዎች፣ ያረጁ ፎጣዎች፣ የተንሻፈፉ ነጠላ ጫማዎች፣ እድሜ የተጫናቸው ሠራተኞችና ተራ ጠባቂ ደንበኞች በብዛት የሚገኙበት ሥፍራ ነው-ፍልውሃ፡፡ ከህመማቸው ለመፈወስና፣ የሻወር አገልግሎት ለማግኘት ከፍቅረኞቻቸው፣ ከባለቤቶቻቸውና ከቤተሰቦቻቸው ጋር ለመታጠብ በርካቶች ወደ ፍልውሃ ይሄዳሉ፡፡ ድርጅቱ የሃያ አራት ሰዓት አገልግሎት የሚሰጥ ቢሆንም ሥፍራው ሁልጊዜም በደንበኞች እንደተጨናነቀ ነው፡፡
በንጉሡ ዘመን ተሰርተው አገልግሎት መስጠት የጀመሩት ክፍሎች፤ እርጅና ተጫጭኗቸውና እድሣት ናፍቋቸው ዛሬም ድረስ ደንበኞቻቸውን እያገለገሉ ይገኛሉ፡፡
ሥፍራው ለአዲስ አበባ ከተማ ምሥረታም ያበረከተው አስተዋፅኦ በቀላሉ የሚገመት አይደለም፡፡ እቴጌ ጣይቱ ከእንጦጦ ቤተመንግስታቸው ተነስተው ወደእዚህ ሥፍራ ለመውረዳቸው ምክንያታቸው በአካባቢው የተፈጥሮ ፍልውሃ መገኘት ነበር፡፡ እቴጌይቱ በፍልውሃ አካባቢ ውበት ተማርከው ጊዜያዊ ማረፊያቸው ካደረጉት በኋላ፣ በሥፍራው በሚገኘው የተፈጥሮ ፍልውሃ መታጠብ የየዕለት ተግባራቸው ሆነ፡፡ አካባቢውን ወደዱት፡፡ በፍልውሃው ፍቅር ወደቁ፡፡ ይህ ደግሞ ባላቸውን (አፄ ሚኒሊክን) አሣምነው የአገሪቱን መናገሻ ከተማ እስፍራው ላይ ለመቆርቆፍ እንዲችሉ ማድረጉን የታሪክ ድርሳናት ያወሳሉ፡፡
ኢትዮጵያ የተፈጥሮ ፍልውሃዎችን በብዛት ከታደሉት አገራት መካከል አንዷ ናት፡፡ ለዚህ ደግሞ ምክንያቱ የምሥራቅ አፍሪካው ታላቁ ስምጥ ሸለቆ የአገሪቱን አብዛኛውን ክፍሎች አቋርጦ የሚያልፍ በመሆኑ ነው፡፡ የአዲስ አበባው ፍልውሃ፣ የሶደሬው አባድር፣ ወንዶገነት፣ ወሊሶና አምቦ ኢትዮጵያ ሆቴል የተፈጥሮ ፍልውሃ ከሚገኝባቸው የአገራችን አካባቢዎች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ እነዚህ የተፈጥሮ ፀጋዎችም ከቱሪዝም መስህብነታቸው እና ከገቢ ማስገኛ ምንጭነታቸው በተጨማሪ ለፈውስ አገልግሎት እየዋሉ ነው፡፡ በፍልውሃው አማካኝነት በርካቶች ከያዛቸው ደዌ እንደሚፈወሱ እንሰማለን፡፡ የጥንት አባቶቻችን ለዘመናት ያለ ሳይንሳዊ ዕውቀት ሲጠቀሙበት የኖሩት ይኸው የተፈጥሮ ፍልውሃ፤ አሁን ዘመናዊና ሣይንሣዊ በሆነ መንገድ ጥናትና ምርምር እየተደረገበት ይገኛል፡፡
የተፈጥሮ ፍልውሃን በማጥናት ሥራ ላይ ተጠምደው የሚውሉ ተመራማዎች አሁን አዲዲስ የጥናትና የምርምር ውጤቶችን ይፋ እያደረጉ ነው፡፡ በቅርቡ በአሜሪካ የሚገኙ ተመራማሪዎች ይፋ ያደረጓቸው መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፤ ከ37°C (ከሰላሣ ሰባት ድግሪ ሴንትግሬድ) እስከ 39°C ድረስ ሙቀት ያለው የተፈጥሮ ፍልውሃ ለጤና እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ ማንኛውም ጤናማ ሰው ቢያንስ በሣምንት አንድ ቀን በዚህ የሙቀት መጠን ውስጥ ባለ የፍልውሃ መታጠብ ወይም መዘፍዘፍ ይኖርበታል፡፡ ይህም በምግብ ውስጥ በበቂ ሁኔታ ልናገኛቸው የማንችላቸውን ንጥረ ማዕድናትንና የተለያዩ ለሰውነት እጅግ አስፈላጊ የሆኑ ማግኒዚየም፣ ሶዲየምና ካልሲየም የተባሉ ማዕድናትን ለማግኘት ያስችለናል፡፡ እነዚህ ማዕድናት ደግሞ ለተለያዩ በሽታዎች ፈውስ እንደሆኑ የህክምና ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡
የተፈጥሮ ፍልውሃዎች እንደሚገኙበት ሥፍራ በማዕድን ይዞታቸው መጠንና በአሲዳምነታቸው እንደሚለያዩ የጠቆመው ይኸው ጥናት፤ በውሃው ውስጥ የሚገኙት ማዕድናት የሚሰጡትም የፈውስ አገልግሎት እንደየሁኔታው ሊለያይ እንደሚችል አረጋግጧል፡፡
የተፈጥሮ ፍልውሃን ፈዋሽነት በሚያጠናው ባላኒዮሎጂ (Balaneyology) በተሰኘው የጥናትና ምርምር ዘርፍ የተሰማሩ የአሜሪካ ሳይንቲስቶች ባደረጉት መረጃ፤ ፍልውሃ በሁለት የተለያዩ መንገዶች ሊገኝ ይችላል፡፡ የመጀመሪያው (Filtrate hot spring) የተባለውና በመሬት ስንጥቅ አማካይነት ወደ ከርሰ ምድር ውስጥ የገባው የዝናብ ውሃ እጅግ ሞቃታማ በሆነው የመሬት ክፍል ውስጥ ደርሶ፣ በውስጡ ከሚገኙ የከርሰ ምድር ማዕድናት የያዘው ሞቃት ውሃ፣ በመሬት ውስጣዊ ግፊት አማካኝነት ወደ መሬት ገፅ በመውጣት በፍል ውሃነት ይከሰታል፡፡ ሌላው የተፈጥሮ ፍልውሃ (Primary hot spring) የተባለው ሲሆን ይህ ውሃ የሚፈጠረው በተፈጥሮ በከርሰ ምድር ውስጥ በሚደረግ እንቅስቃሴ ነው፡፡ በከርሰ ምድር ውስጥ በሚደረግ እንቅስቃሴ አማካኝነት በርካታ ማዕድናትና ንጥረ ነገሮች ከውሃው ጋር ይቀላቀላሉ፡፡ በመሬት ግፊትም ውሃው ወደ ገፀ ምድር ሲወጣ በርከት ያሉ ለጤና እጅግ ጠቃሚ የሆኑ ማዕድናትንና ንጥረ ነገሮችን ይዞ ይወጣል፡፡ በሁለቱ የተለያዩ መንገዶች የሚገኘው ፍልውሃ፤ የተለያዩ የማዕድንና የጋዝ መጠኖች ያሉት ሲሆን የሶዲየም ክሎራይድ ይዘትም አለው፡፡ ከ3-5% የሚደርስ የሶዲየም ክሎራይድ ይዘት ያለው የተፈጥሮ ፍልውሃ፤ ለመገጣጠሚያ ብግነት፣ ለቁርጥማት ለነርቭ በሽታ፣ ለአጥንት መሳሳት፣ ለጡንቻ መተሳሰር እና መሰል የጤና ችግሮች መድሃኒት መሆኑን ጥናቶች አረጋግጠዋል፡፡
የተፈጥሮ ፍልውሃ ከዚህ በተጨማሪ ለቆዳ በሽታዎች፣ ለመተንፈሻ አካላት ችግሮች እፎይታን ይሰጣል፡፡ የአዕምሮን የማሰብ ችሎታ ከፍ ለማድረግ፣ ድብርት ሲጫጫነን፣ ጤናማ የልብ ምት እንዲኖረን፣ ሰውነታችን ውስጥ የሚፈጠሩ መርዛም ንጥረ ነገሮችን ለማስወገድና የሆርሞን ስርዓታችንን ለማስተካከል የተፈጥሮ ፍልውሃዎች ከፍተኛ ጠቀሜታ አላቸው፡፡
ከከርሰ ምድር የሚገኙት የተፈጥሮ ፍልውሃዎች በሚኖራቸው የሙቀት መጠን እንደሚለያዩ መረጃው ጠቁሞ፤ በዚሁ የሙቀት መጠናቸው ልክም በአራት የተለያዩ መደቦች እንደሚከፈሉ ገልጿል፡፡ የሙቀት መጠናቸው ከ25°C በታች የሆኑና ከከርሰ ምድር የሚገኙት ቀዝቃዛ የምንጭ ውሃ (Cold Spring water) ሲባሉ፣ የሙቀት መጠናቸው ከ25-34°C ድረስ ያሉት ደግሞ ለብ ያለ (Tepid Spoizing Spring water) ይባላሉ፡፡ ከ34-42°C ድረስ ያሉት የገፀ ምድር ውሃ ሞቃታማ (Warm Spring water) በሚል መጠሪያ ሲታወቁ ከ42°C በላይ ያሉት ደግሞ ፍልውሃ (hot Spring water) ተብለው ይጠራሉ፡፡
ከላይ ለመግለፅ እንደሞከርነው እነዚህ የተለያየ የሙቀት መጠን ያላቸው የተፈጥሮ ፍልውሃዎች፤ እንደሙቀት መጠናቸውና እንደማዕድን ይዘታቸው የሚሰጡት የፈውስ አገልግሎትም ይለያያል፡፡ የሙቀት መጠናቸው ከፍ ያለ ፍልውሃዎች እንፋሎታቸው ከባድ በመሆኑ የደም ግፊት፣ የልብ ድካም፣ የካንሰር፣ የጉበትና የኩላሊት ህሙማንና ነፍሰጡር ሴቶች ባይጠቀሙ ተመራጭ እንደሆነ የጤና ባለሙያዎች ይመክራሉ፡፡

*መጠለያው ሲሰራ ሁሉም ይሰጣቸዋል ማለት አይደለም፤ ይገባቸዋል ያልናቸውን ለይተናል
*ወረዳው ለትራንስፖርት ያወጣውን ገንዘብ ከፍለው እቃቸውን መውሰድ ይችላሉ

ባለፈው ሳምንት “ትራሳቸውን ቤተመንግስት ፤ ግርጌያቸውን ሸራተን ያደረጉ ቤት አልባዎች” በሚል ርዕስ በሸራተን አካባቢ ለመልሶ ማልማት በታጠረው ቤተ-መንግስቱ ሥር ባለው ቦታ በላስቲክ ቤት ውስጥ ስለሚኖሩ 48 አባወራዎችና ቤተሰቦቻቸው አስከፊ ህይወት ሰፋ ያለ ዘገባ ማቅረባችን ይታወሳል፡፡ በወቅቱ የወረዳውን ሃላፊዎች ማግኘት ባለመቻላችን በጉዳዩ ዙሪያ ምላሻቸውን ማካተት አልቻልንም፡፡ በዚህ ሳምንት የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ተስፋዬ ፣በአራዳ ክፍለ ከተማ የወረዳ ስምንት ዋና ስራ አስፈፃሚ ወ/ት ህይወት ጉግሳን አነጋግራ የሰጡትን ምላሽ አቅርበናል፡፡


በወረዳችሁ 48 አባዎራዎች ከነቤተሰባቸው ቤተመንግሥቱ ሥር በላስቲክ ቤት ውስጥ እንደሚኖሩ ታውቃላችሁ?
እናውቃለን፡፡ ቁጥራቸው ከ48 አባወራዎች ይበልጣል የሚል ግምትም አለን፡፡
እነዚህ ሰዎች በቀድሞው ቀበሌ 22 ውስጥ ከ17-23 ዓመት መኖራቸውንና ቦታው ለልማት ሲፈለግ ቤት አልባ እንደሆኑ ገልጸውልናል፡፡ የቀበሌ መታወቂያ ያላቸውም አሉ፡፡ የእነዚህ ሰዎች እጣ ፈንታ ምንድን ነው?
በመነሻነት ሁሉም ህጋዊ ባለይዞታዎች አልነበሩም፡፡ ቦታው ለመልሶ ማልማት ሲፈለግ ምትክ የሚሰጠው ባለይዞታ ለነበሩ ሰዎች ነው፡፡ ይህን የመልሶ ማልማት መመሪያን በተከተለ መልኩ ለባለይዞታዎች ምትክ ቦታ ሰጥተን አጠናቀናል፡፡
ታዲያ እነዚህ ነዋሪዎች ለበርካታ ዓመታት የት ነው የኖሩት?
እነዚህ ሰዎች በጥገኝነትና በተከራይነት አብረው የኖሩ ናቸው፤ ለምሳሌ በአንድ ቤት ቁጥር ስሜ ተመዝግቦ ባለይዞታ ከሆንኩ ምትክ ቤቱን የማገኘው እኔ ነኝ፡፡ ከዚያ በኋላ ያከራየኋቸውንም ሆነ ያስጠጋኋቸውን አብሬ ይዤ መሄድ አለብኝ ማለት ነው፡፡ ከላይ እንደነገርኩሽ ወረዳው የመልሶ ማልማት ስራ የተከናወነበት እንደመሆኑ ምትክ ለሚሰጣቸው ምትክ ሰጥተን ጨርሰናል፡፡ አሁን በላስቲክ ቤት ውስጥ የሚኖሩት ከቤተሰቦቻቸው ጋር ይኖሩ የነበሩ ናቸው፡፡ ለምሳሌ አንድ ልጅ ከቤተሰቡ ይዞታ ጐን ላይ ትንሽ ቤት ይሠራና እዚያው አግብቶ ይወልዳል፣ ከዚያ ለእኔም ቤት ይገባኛል ይላል፤ ይሄ የማይሆን ነገር ነው፡፡ ወረዳው ይህን ሰው የሚያውቀው ከቤተሰቡ ጋር ነው፣ ስለዚህ ቤተሰቡ ቤት ሲያገኝ አብሮ መሄድ ነው ያለበት፡፡
ወረዳው ታዲያ እነዚህ ዜጐች ምን እንዲሆኑ ያስባል?
እኛ ከፖሊስ ጋር ጭምር እየገባን እርምጃ ለመውሰድ ሞክረናል፣ ምክንያቱም ቦታው ለፀጥታ ስጋት እስከመሆን ደርሷል፡፡
ምን አይነት እርምጃ?
ከቦታው እንዲነሱና ወዳስጠጓቸው ወይም ወደ ቤተሰቦቻቸው እንዲቀላቀሉ ለማድረግ ሞክረናል፡፡ ቀደም ሲል እንደነገርኩሽ፣ አንዳንዶቹ “እኛም ቤት እናገኛለን” በሚል ከቤተሰቦቻቸው ተነጥለው የቀሩ ናቸው፡፡ ቤት ላንሰጣቸው፣ህጋዊ ባለይዞታ ላይሆኑ፣ ላስቲክ ወጥረው መኖርና መስራት እየቻሉ ወደ ልመና ማዘንበል አግባብ ነው ብሎ ወረዳው አያምንም፡፡ አሁን ተጠግቶ ለሚኖርና 18 ዓመት ለሞላው ሁሉ ቤት ለመስጠት የምንችልበት ደረጃ ላይ አይደለንም፡፡ በነገራችን ላይ በፊት በላስቲክ ቤት የሚኖሩት እነዚህ ብቻ አልነበሩም፤ በጣም ከፍተኛ ችግር ላለባቸው፣ የነበሩበት ሁኔታ በነዋሪዎች ኮሚቴና በአስተዳደር አካላት ተጣርቶ በተወሰነ መልኩ እንዲስተናገዱ ተደርጓል፡፡
በምን መልኩ ተስተናገዱ? ቁጥራቸውስ ምን ያህል ነው?
ቁጥራቸውን እርግጠኛ ባልሆንም ከ25 በላይ የሆኑና አደጋ ላይ ሊወድቁ ይችላሉ ተብለው የተመረጡ ሰዎች፣ የቀበሌ ቤትና መጠለያ ተሰርቶላቸው መፍትሔ አግኝተዋል፡፡ አሁን ያሉትን ሁሉ ለማስተናገድ ከአቅም በላይ ነው፡፡ በእርግጥ ቦታው ላይ ሆነሽ ስታያቸው፣ ህይወታቸው ሊያሳዝን ይችላል፡፡ ግን ቤተሰብ ስለሆኑ ብቻ ቤት ልስጥ ማለት አይቻልም፡፡ መመሪያ መጠበቅ አለበት፡፡
ባለይዞታ ባይሆኑም በስማቸው ቤት ባይኖራቸውም ቀደም ሲል ግን እዚሁ ቀበሌ ውስጥ የሚኖሩ ነበሩ፡፡ እንደዜግነታቸው መፍትሔ አያሻቸውም?
በነገራችን ላይ ለእነዚህም መፍትሔ እየተፈለገላቸው ነው፡፡ ቦታ ያልተሰጣቸው ህጋዊ ስላልሆኑ ነው፡፡ ለረጅም ጊዜ ኖረናል ይላሉ፣ ግን ሲኖሩ የነበረው ቀደም ሲል በነገርኩሽ አግባብ ነው፡፡ ከቤተሰባቸው ቤት ጐን ጠግነው፣ ተከራይተውና ተጠግተው ማለት ነው፡፡ እነዚህን ነገሮች ሁለት ሶስት ጊዜ አጣርተናል፡፡ “ወረዳው ነው የከለከለን፣ ክፍለከተማው ጉዳያችንን ይይልን” ብለው ወደ ክፍለ ከተማ ሄደው፣ ኮሚቴ ተዋቅሮ ጉዳዩ ታይቷል፡፡ ክፍለከተማውም ያገኘው ከእኛ መረጃ ውጭ አይደለም፡፡ አንድም እናትና አባቱ ሄደው ልጅ ነው የቀረው፡፡ እናም ወልጃለሁ፣ ቤተሰብ አለኝ ቤት ይገባኛል ነው የሚለው፣ አሊያም እንደአቅሜ በ30 ብር ተከራይቼ ረጅም አመት ኖሬያለሁ የሚሉ ናቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች በአነስተኛና ጥቃቅን ተደራጅተው ስራ በመስራት፣ ኑሯቸውን እንዲለውጡ ወርደን እስከማማከር ደርሰናል፡፡ ከዚህ ውጪ ምትክ ቤት የምንሰጥበት አግባብ የለም፡፡ መመሪያውም ህጋዊ ተነሺዎች ስላልሆኑ አይደግፋቸውም፡፡
እነዚህ ሰዎች ግን በጊዜው ወደ ወረዳው እየመጡ አቤቱታ ሲያሰሙ “ቤት እንሰራላችኋለን” እንዳላችኋቸውና ለዚህም የማረጋገጫ ወረቀት እንደተሰጣቸው ይናገራሉ፡፡ እንዴት ነው?
ደብዳቤ ተሰጥቶናል የሚሉት ፍፁም እውነት ያልሆነና የተሳሳተ መረጃ ነው፡፡ እንሰራላችኋለን ብሎ ቃል የገባላቸው ወይም ለዚህ ማረጋገጫ ደብዳቤ የሰጣቸው አካል የለም፡፡ በእርግጥ በአንድ ወቅት “ስራ አጥ ስለመሆናችን ደብዳቤ ስጡን” ብለው የተሰጣቸው ደብዳቤ እጃቸው ላይ አለ፡፡
የቤት እቃቸው፣ የልጆቻቸው ልብስ ሳይቀር ተጭኖ መጥቶ ወረዳው ግቢ ውስጥ ዝናብ እያበሰበሰው እንደሆነ እነዚህ ሰዎች ይናገራሉ፡፡ እኛም የተወሰነ እቃ እዚሁ ግቢ ውስጥ ተመልክተናል፡፡ የልጆች ልብስና የመመገቢያ እቃ አጥተው መቸገራቸውን ገልፀውልናል፡፡ ይሄስ እውነት ነው?
እቃቸውን በተመለከተ ትክክል ናቸው፣ እዚህ ቀበሌ ግቢ ውስጥ አለ፡፡ ግን ተነጥቀው አይደለም የመጣው፡፡ አሁንም እንወስዳለን ካሉ የሚከለክላቸው የለም፡፡ እቃቸው የተጫነበት ምክንያት በቦታው ሰፊ የፀጥታ ችግር ነበር፡፡ መነሻውም ቤት ካልተሰጠን አንለቅም የሚል ነው፡፡ በዚህ የተነሳ የተፈጠረውን የፀጥታ ችግር ለማርገብ፣ ከፖሊስ ጋር በትብብር ቦታው ድረስ ወርደን አነጋገርናቸው፡፡ “ህጋዊ ባለይዞታ ባልሆናችሁበት አግባብ ምትክ ይሰጠን ማለት አትችሉም፣ እንደማንኛውም ችግረኛ መጠየቅ ካለባችሁ በረብሻ ሳይሆን ወጥታችሁ ነው መጠየቅ ያለባችሁ” የሚል አቅጣጫ ሰጠናቸው፣ ነገር ግን ከችግራቸው በመነሳት “ቤት ካልሰጣችሁን፣ እንዲህ ካላደረጋችሁልን፣ ከእቃችን ጋር እዚሁ አጥፉን፣ አንቀሳቀስም” የሚል ጫፍ ያዙ፡፡ አሁን እንኳን ሄደን ብናናግራቸው ከዚህ የተለየ ነገር አይሉም፡፡
እኮ ከዚህ ወጥተው የት ይሂዱ? ወረዳውስ ምን አማራጭ አስቀመጠላቸው?
ወረዳው ህጋዊ ባለይዞታ ላልሆኑ አማራጭ የማስቀመጥ ግዴታ የለበትም፡፡ መመሪያውም ይህን አይፈቅድም፡፡ በዚህ የተነሳ እቃ ሊያነሱ አልቻሉም፡፡ ጭራሽኑ የበለጠ ያደራጁ ጀመር፡፡ እኛ ደግሞ መሬቱን ለመሬት ልማት ባንክ ማስረከብ ነበረብን፡፡ ምክንያቱም ቦታው ለገዛው ባለሀብት ስለሚውል ማለት ነው፡፡ እነሱ ግን ብዙ ቤተሰብና እቃ በመሰብሰብ ቤት እናገኛለን የሚል ወደ የዋህነት ያዘነበለ አስተሳሰብ ይዘዋል፡፡ ይህ ደግሞ የትም አያደርሳቸውም፡፡ በዚህ ምክንያት እቃቸውን ጭነን ወስደናል፡፡
ቀደም ሲል መውሰድ ከፈለጉ አሁንም መውሰድ ይችላሉ ብለሻል፡፡ መጀመርያ ለምን ተወሰደ? ይውሰዱ ከተባለስ--- “ውሃ ቅዳ ውሀ መልስ” ለምን አስፈለገ?
እንደነገርኩሽ ቦታውን ማስለቀቅ ነበረብን፡፡ እቃቸው ሲወሰድ ይነሳሉ በሚል ነበር የተጫነው፡፡ እነሱ ሊለቁ አልቻሉም፡፡ ሆኖም በጣም አስፈላጊ አስፈላጊ እቃዎችን፣ አንገብጋቢ ለሆነ ችግር የሚፈልጉትን እየመጡ እንዲወስዱ ነገርናቸው፣ እየወሰዱም ነው፡፡ ሙሉ እቃቸውን መውሰድ ከፈለጉ ግን ወረዳው ለትራንስፖርት ያወጣውን ወጪ ከፍለው መውሰድ ይችላሉ፡፡ የመጫኛ ጉልበት ራሳቸው ስለጫኑ አናስከፍላቸውም፡፡
እቃቸው ተጭኖ መወሰዱ ምን መፍትሄ አመጣ?
በወቅቱ መፍትሄዎችን አግኝተናል፡፡ ለምሳሌ እቃቸውን በማንሳታችን ምክንያት ቦታውን ለማስረከብ ስንነሳ፣ የወጠሩትን ላስቲክ ብቻ ለማፍረስ ቀላል ሆኖልናል፡፡
ማፍረስ ብቻ ሳይሆን ለስምንት ጊዜ ያህል ላስቲክ ቤቱን አቃጥላችኋል፣ ስታቃጥሉም ከሌሊቱ ስምንትና ዘጠኝ ሰዓት እየሄዳችሁ እንደሆነ ሰምተናል፡፡ ያንን ስታደርጉ ህይወት ቢጠፋ ንብረት ቢወድም ተጠያቂው ማን ነበር?
የላስቲክ ቤት ቃጠሎው የተካሄደው እነሱ ላይ ጉዳት በሚያደርስ መልኩ አይደለም፡፡ ከሌሊቱ ስምንት ዘጠኝ ሰዓት አቃጠሉብን የሚለው የተሳሳተ መረጃ ነው፡፡ ምክንያቱም የመንግስት የስራ ሰዓትም አይደለም፡፡ ከጠዋቱ 2፡30 እስከ 11፡30 ባለው ነው የምንሰራው፡፡ ሌላው ቀርቶ 12 ሠዓት ላይ እንኳን ሄደን አናስጨንቃቸውም፡፡ ሶስት አራት ጊዜ ወርደን አቃጥለናል፡፡ ትክክል ነው፡፡ በትክክል ካሰብነው ያሉበት ቦታ ለራሳቸው ለጤናቸውም አስቸጋሪ ነው፡፡
ግን እኮ ወደው አይመስለኝም ፡፡ አማራጭ ስላጡ ነው፡፡ ድሮ እነዚህ ሰዎች በ30 ብር ቤት ኪራይ ያገኙ ነበር፡፡ አሁን በ400 ብርም የለም፡፡ እንዴት ይሁኑ?
ልክ ነው ግን ከላስቲክ ቤቱ ቃጠሎ ለመጀመር፣ መጀመሪያ በአግባቡ ተነግሯቸዋል፣ ህጋዊ ባለይዞታ ስላልሆኑና እንዲህ አይነት ድርድርም ውስጥ መግባት ስለሌለብን፣ አስጠንቅቀን ጉዳት ሳይደርስባቸው ነው ያደረግነው፡፡ ይሄ በህግና በመመሪያ የሚተዳደር አገር ነው፣ ነገ ሌሎች የልማት ቦታዎች ላይ ሄደው ሰፍረው “አንወጣም ግደሉን” ማለት ይመጣል፡፡ ስለዚህ ቃጠሎው ከመምጣቱ በፊት ሶስትና አራት ጊዜ መድረክ ተመቻችቶ በደንብ ተነግሯቸዋል፡፡ ግን ሊሠሙ አልቻሉም፡፡ በዚህ የተነሳ ቃጠሎውን አከናውነናል፡፡ በሌሊት የተባለው ውሸት ነው፡፡ በሰው ላይ ጉዳት አላደረስንም፤ እኛ እንደውም ይህን ስናደርግ አማራጭ ዕድሎችን ይፈልጋሉ በሚል ነበር፡፡
ምን አይነት አማራጮችን?
ለምሳሌ አብዛኛው ወጣት ነው፤ የጉልበት ስራ፣ ኮብልስቶን፣ የብሎኬት ምርት ስራና በመሳሰሉት ተደራጅተው መስራትና የልመናን አስተሳሰብ ያስወግዳሉ፤ ከዚያም እንደየአቅማቸው ቤት ይከራያሉ ብለን ነበር፤ግን አልሆነም፡፡
መስራት የማይችሉ አቅመ ደካሞችና ህሙማን ጉዳይስ እንዴት ይታያል?
አቅመ ደካሞች ማለትም 70 እና 80 አመት የሆናቸው በጣት የሚቆጠሩ ናቸው፡፡ ሌላው ሰርቶ ለመኖር የሚያስችል አቅም አለው የሚል እምነት አለን፡፡ ይህን የፈጠረው ለስራ ያላቸው የወረደ አመለካከት ነው፡፡
ታዲያ ይህን የተዛባ አመለካከት የመቀየርና ህብረተሠቡን የማንቃት ሀላፊነት የማን ነው?
እኛ ብዙ ጊዜ ልናስተምራናቸው ሞክረናል ግን ወደ ልመና ያዘነብላሉ፡፡ ድሮም ተከራይተውና ተጠግተው ሲኖሩ ይሠሩ ነበር፤ አሁን እንደውም ከላይ የገለፅኳቸው አማራጭ ስራዎች አሉ፡፡ ከእነሱ መካከል ምክራችንን ሰምተው በብሎኬት ምርትና በኮብልስቶን የተሰማሩ አሉ፡፡ ወደፊትም አመለካከታቸውን ለመለወጥ ጥረታችንን አናቆምም፡፡
ቁርጥ ያለውን ንገሪኝ ፤ በአጭሩ ወረዳው እንደመፍትሔ የያዘው ሃሳብ አለው ?
አሁን ባለው ሁኔታ መንግስት ማንም ጐዳና እንዲወጣ አያበረታታም፤ እስከመጨረሻው የምንመክራቸው ወደ ቤተሰቦቻቸው ሊገቡ የሚችሉበት እድል ስላለ እሱን መጠቀም አለባቸው፡፡ ይህን በተጨባጭ ያውቃሉ፡፡ እኛም እናስተምራቸዋለን፡፡ ይሄ አንዱ ነው፡፡ ሁለተኛው፤አሁን መሬት ያልረገጠ ነገር ማውራት ጥሩ አይደለም እንጂ ጊዜያዊ ማረፊያ የማዘጋጀት ጉዳይ ለክፍለ ከተማው አቅርበን ሃሳቡ ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ ሃሳቡ እንዴት ተግባራዊ እንደሚሆን እየታየ ነው፡፡ ወረዳው እንደ አጠቃላይ ሃሳብ ያየው ነገር፤ ህጋዊ ባለይዞታ አይደሉም፣ አዎ አይደሉም፣ ነገር ግን በቦታው ላይ በምንም መልኩ ቢሆን ልጅ ወልደው ቤተሰብ መስርተው በመኖራቸው ለማህበራዊ ቀውስ ተዳርገዋል ያላቸውን ሰዎች ለይቷል፣ በነገራችን ላይ ከነዚህ ሰዎች ጋር ቤት አገኛለሁ ብለው ከጐዳና ገብተው የተቀላቀሉም አሉ፡፡ የመፍትሔ ሃሳብ ስናዘጋጅ፣ በወረዳችን ክፍት የሆነ ቦታ እና ለጊዜያዊ መጠለያ ግንባታ ሊሆን ይችላል ያልነውን አየንና መነሻ ሃሳቡን ለክፍለከተማው አቀረብን፡፡ ክፍለከተማው፣ ወረዳው ያየበት አግባብ ጥሩ ነው በሚል ተቀብሎታል፡፡ ይህም ቢሆን በዜግነታቸው እንጂ በአሁኑ ወቅት መጠለያ የሚመከር ጉዳይ አይደለም፡፡ በዚህ ደረጃ ነው ያለው፡፡ ቦታው በመሀንዲሶች ይታያል፣ የግንባታው አይነትና ሁኔታ ምን ይምሰል የሚለው ይወሰናል፣ መሬቱ የሚፀድቅበት መንገድና አጠቃላይ ነገሮች ታይተው የሚሆነው ይሆናል፡፡
እነዚህ ሰዎች በዚህ ሁኔታ ህይወታቸውን መግፋት ከጀመሩ አምስተኛ አመታቸውን ይዘዋል፡፡ መጠለያውን ለማግኘትስ ምን ያህል ጊዜ ይወስድ ይሆን?
ቦታው ለልማት በአስቸኳይ ይፈለጋል፡፡ ቦታውን ለማስረከብ ደግሞ እነዚህን ሰዎች ቦታ ማስያዝ አለብን፡፡ ስለዚህ ከዚህ በኋላ ረጅም ጊዜ ይወስዳል ብዬ አላስብም፡፡ እዚህ ላይ ማስመር የምንፈልገው፣ ነገሩ እውን ሆኖ ጊዜያዊ መጠለያው ሲሰራ፣ እዚያ ያሉት ሰዎች ሁሉ ያገኛሉ ማለት አይደለም፣ ይገባቸዋል ያልነውን ለይተን አስቀምጠናል፡፡

አንድ ባቡር በአንድ ጉዞ ከ300 በላይ ተጓዦችን ያሳፍራል
. ባቡሩ 80 ኪሎ ሜትር በሠአት የመብረር አቅም ይኖረዋል
. በአፍሪካ የከተማ ባቡር ተጠቃሚዎች ሰባት ብቻ ናቸው

የአዲስ አበባ ከተማ ቀላል ባቡር ፕሮጀክት በሁለት ምዕራፎች ተከፍሎ የሚከናወን ሲሆን በጠቅላላው 32 ኪሎ ሜትር ገደማ የሚደርሠው የመጀመሪያው ምዕራፍ ግንባታ፣ በ2007 ዓ.ም መጨረሻ ላይ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ይጀምራል፡፡ ሁለተኛው ዙር ፕሮጀክት፤ የባቡር መስመር ዝርጋታውን ወደ 75 ኪሎ ሜትር የሚያደርስ ሲሆን ይህ የማራዘሚያ ፕሮጀክት የሚከናወነው በ2006 ዓ.ም ነው፡፡ 
አሁን በግንባታ ሂደት ላይ የሚገኘው የመጀመርያ ምዕራፍ የባቡር መስመር ዝርጋታ መነሻው ሃያት ሲሆን በመገናኛ፣ 22፣ ኡራኤል፣ መስቀል አደባባይ፣ ሜክሲኮና ልደታ አድርጐ ጦር ሃይሎች የሚደርስና የ16.3 ኪ.ሜ ርዝመት ያለው ነው፡፡ ከሠሜን ወደ ደቡብ የሚጓዘው ደግሞ መነሻው ከፒያሣ (ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን) ሆኖ በአዲስ ከተማ፣ አውቶቡስ ተራና 7ኛ አድርጐ፣ ከጦር ሃይሎች ከሚመጣው መስመር ጋር በጥምረት እስከ መስቀል አደባባይ ከመጣ በኋላ እስከ ቃሊቲ ማሠልጠኛ አደባባይ የሚዘልቅና የ17.5 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው ነው፡፡
በኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ፕሮጀክት ስራ አስኪያጅ ኢ/ር በሃይሉ ስንታየሁ፤ ስለባቡር መስመር ዝርጋታው፣ ስለባቡሮቹ አቅምና የቴክኖሎጂ ደረጃ፣ እንዲሁም ስለፌርማታና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ተጠይቀው የሠጡትን ምላሽ ጠቅለል አድርገን በሚከተለው መልኩ አጠናቅረነዋል፡፡

የባቡሮች አቅም እና የአገልግሎት ዘመን
የፕሮጀክቱ ምዕራፍ አንድ ሲጠናቀቅ 41 ባቡሮች ወደ አገልግሎት ይሠማራሉ፡፡ አንድ ባቡር 3ዐ ሜትር ርዝመት ያለው ሲሆን ይህም ማለት ከሁለት ባለ ተቀጣጣይ የቢሾፍቱ አውቶብሶች ርዝማኔ ላይ 6 ሜትር ብቻ መቀነስ ማለት ነው፡፡ የአንዱ ተቀጣጣይ አውቶቡስ ርዝመት 18 ሜትር ሲሆን የሁለት አውቶብሶች ሲደመር 36 ይሆናል፡፡ በባቡሩ ውስጥ 64 መቀመጫዎች ብቻ ይኖራሉ፡፡ እነዚህ ወንበሮች ለአቅመ ደካሞችና ለአካል ጉዳተኞች እንዲሁም ለረጅም ርቀት ተጓዦች የተሠናዱ ሲሆን አብዛኛው ተጠቃሚ ቆሞ እንዲሄድ ይጠበቃል፡፡ በአንድ ካሬ ሜትር ውስጥ ከ6-8 ሠው ሊቆም ይችላል በሚል ሲሠላ፣ በአጠቃላይ አንድ ባቡር በአንድ ጉዞ ከ268 እስከ 317 ሠዎችን ማጓጓዝ ይችላል ማለት ነው፡፡ በዚህ አይነት በሁለቱ አቅጣጫ የሚጓዙት ባቡሮች፣ በጋራ በሚጠቀሙት ከልደታ እስከ መስቀል አደባባይ ባለው መስመር እስከ 15ሺህ ሠው በአንድ ሠአት ውስጥ ማጓጓዝ የሚቻል ሲሆን በተናጠል በሚጓዙባቸው መስመሮች ቁጥሩ እስከ 7ሺህ ይጠጋል፡፡
የባቡር መሠረት ልማቱ (ሃዲዱ) በየጊዜው ተገቢው ጥገና እየተደረገለት እስከ መቶ አመት ድረስ እንዲያገለግል ታስቦ ነው የሚሰራው፡፡ ከኤሌትክሪፊኬሽንና ሲግናል (ማመላከቻ) እንዲሁም ከዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ጋር የተያያዙት ደግሞ አስፈላጊው እድሣትና ጥገና እየተደረገላቸው እስከ 40 አመት እንዲያገለግሉ ተደርገው ይሠራሉ፡፡

የባቡር ፌርማታዎች
ከሰሜን ደቡብ፣ ከምስራቅ ምዕራብ በሚዘረጉት እያንዳንዱ መስመር 22 ፌርማታዎች የሚኖሩ ሲሆን በጠቅላላው 39 ፌርማታዎች ይዘጋጃሉ፡፡ ከነዚህ ውስጥ አምስቱ ከልደታ እስከ መስቀል አደባባይ በሚዘልቀው የጋራ መስመር ላይ የሚገኙ ናቸው፡፡ በየፌርማታዎቹ መካከል በአማካይ እስከ 700 ሜትር ርቀት የሚኖር ሲሆን በአንዳንድ ቦታ እስከ 400፣ ረጅም በሆኑት ለምሣሌ እንደጐተራ ማሳለጫ አካባቢ ደግሞ እስከ 1.2 ኪሎ ሜትር ርቀት ይኖራል፡፡ ተገቢው ፌርማታ ጋ ለመድረስ አንድ ተጠቃሚ ከ300 እስከ 400 ሜትር ብቻ በእግሩ መጓዝ ይጠበቅበታል ማለት ነው፡፡
ፌርማታዎቹ ሦስት አይነት ናቸው ይላሉ -ስራ አስኪያጁ፡፡ አንደኛው መሬት ላይ የሚሠራ ፌርማታ ነው፡፡ ሁለተኛው የድልድይ ላይ ፌርማታ ሲሆን ሦስተኛው የመሬት ውስጥ ፌርማታ ናቸው፡፡ የመሬት ላይ ፌርማታ በሚሆንበት ጊዜ፣ ተጠቃሚዎች ለዚሁ አገልግሎት ብቻ በሚሰራ 60 ሜትር በሚረዝም ወለል (ፕላት ፎርም) ላይ ሆነው ይጠብቃሉ፡፡
ጀድልድይ ፌርማታ ደግሞ ከድልድዮቹ በቀጥታ በግራና ቀኝ በኩል ወደ እግረኞች መንገድ ዳር የሚወርዱ የመተላለፊያ ደረጃዎችና ሊፍቶች ይኖራሉ፡፡ አንድ ሰው በድልድዩ ፌርማታዎች መጠቀም ከፈለገ፣ በአስፓልቱ ዜብራዎች በኩል በእግሩ ግራና ቀኝ አስፓልቱን አቋርጦ፣ ደረጃው ጋ ከደረሰ በኋላ ከፈለገ በደረጃው፣ ካሻውም በሊፍቱ ሽቅብ ወደ ድልድዩ መውጣት ይችላል፡፡ በተለይም አቅመ ደካሞችና አካል ጉዳተኞች ሊፍቱን እንዲጠቀሙ ቅድሚያ ይሰጣል፡፡
በመሬት ውስጥ ፌርማታዎችም በሁለቱም አቅጣጫ ወደ ውስጥ የሚያስገቡና የሚያስወጡ ደረጃዎች እና ሊፍቶች ይኖራሉ፡፡ በዚያ መሠረት ሁሉም ሰው የሚመቸውን አማራጭ በመጠቀም ወደ ውስጥ መግባትና መውጣት ይችላል፡፡

የባቡሮቹ ፍጥነትና የቴክኖሎጂ ደረጃቸው
የመጀመያው ምዕራፍ ግንባታ በ2007 ዓ.ም ከተጠናቀቀ በኋላ ወደ አገልግሎት ይገባሉ ተብለው የሚጠበቁት ባቡሮች፤ በሰአት 80 ኪሎ ሜትር የመብረር አቅም እንዲኖራቸው ተደርገው ዲዛይን የሚደረጉ ሲሆን ወደ አገልግሎት ሲሰማሩ ግን በአማካይ በየ700 ሜትር ርቀት ፌርማታ ስለሚኖር ፍጥነታቸው በሰአት ከ30 እስከ 40 ኪሎ ሜትር ዝግ እንዲል ይደረጋል፡፡ የቀላል ባቡር ፕሮጀክቱ በጀት የባቡሮቹን ዋጋም የሚያጠቃልል ነው፡፡ ኮንትራክተሩ ከመከላከያ ኢንጅነሪንግ ጋር በጋራ የሚገጣጥማቸውን ባቡሮች ጨምሮ ከውጭ ተገዝተው የሚመጡ ባቡሮችም ይኖራሉ፡፡
የቴክኖሎጂ ደረጃቸውን በተመለከተ አሁን የብዙሃን ትራንስፖርት አገልግሎት በተስፋፋባቸው ሃገሮች ያለውን የሲግናል (ማመላከቻ)፣ የኮሚኒኬሽንና የኤሌክትሪክፊኬሽን ሲስተም ያሟላ እንደሚሆን ኢንጂነር በኃይሉ ይገልፃሉ፡፡ ለምሳሌ የትኬት አገልግሎት ሲስተሙን ስንመለከት፣ ሁለት አይነት ትኬት ይኖራሉ፡፡ የኤሌክትሮኒክስ እና የወረቀት ትኬቶች፡፡ በዋናነት ጥቅም ላይ የሚውለው የኤሌክትሮኒክ ቲኬቱ ሲሆን ማንኛውም ባቡር ተጠቃሚ ያንን ትኬት ከኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ከገዛ በኋላ፣ በየጊዜው ሂሣብ እያስሞላ መጠቀም ይችላል፡፡ በየቦታው የተዘጋጁ የሂሳብ መሙያ ጣቢያዎችም ይኖራሉ፡፡ ተጠቃሚው ልክ ወደ ባቡሩ ሲገባ፣ በሩ ላይ ወደሚገኘው ትኬት አንባቢ መሣሪያ (SVT Reader) ቲኬቱን በማስጠጋት እንዲነበብለት ያደርጋል፡፡ በቂ ሂሣብ ካለው እንዲገባ ይፈቀድለታል፡፡ ይህን ሂደት የሚቆጣጠሩ መኮንኖችም በባቡሩ ውስጥ ይኖራሉ፡፡ ተጠቃሚው መውረጃው ጋ ሲደርስ በድጋሚ የኤሌክትሮኒክስ ትኬቱን በሩ ጋ ወዳለው አንባቢ መሣሪያ በማስጠጋት እንዲነበብና ለተጓዘባት ኪሎ ሜትር ተገቢው ክፍያ እንዲቆረጥ ያደርጋል፡፡ አንባቢ መሣሪያውም ተጠቃሚው የተጓዘበትን ርቀት አስልቶ ሂሣቡን ይቆርጣል፡፡ አንድ ተሣፋሪ ይህን ሳያደርግ ከወረደ፣ መሣሪያው እስከ መጨረሻው ፌርማታ ድረስ ያለውን ታሪፍ አስልቶ ይቆርጥበታል፡፡ በዚህ ሂደት የባቡሩ ሠራተኞች (መኮንኖች) የት ኬት ማንበቢያ መሣሪያውን በእጃቸው ይዘው ተገቢውን ቁጥጥርና ክትትል ያደርጋሉ፡፡
የወረቀት ትኬቱ በአብዛኛው ከክፍለ ሀገር ለሚመጡና የአጭር ጊዜ ቆይታ ላላቸው የአንድ ጊዜ ተጓዦች የሚዘጋጅ ይሆናል፡፡ የጉዞ ታሪፍ በተመለከተ አሁን የተወሰነ ነገር ባይኖርም የአብዛኛውን ህብረተሰብ አቅም ያገናዘበ ይሆናል ተብሎ ይገመታል፡፡
ባቡሩ ከትኬት አቆራረጥ ዘመናዊነቱ ባሻገር፣ የባቡሩን መነሻና መድረሻ እንዲሁም እያንዳንዱን የሚቆምበትን ፌርማታ ለተሳፋሪዎች በድምጽና በጽሑፍ ያሳውቃል፡፡
ለዚሁ በተዘጋጀው ስክሪን ላይ ቀጣይ ፌርማታ የቱ እንደሆነም ይገልፃል፡፡ በድምጽም ጭምር፡፡ በአሁኑ ወቅት የባቡር ኦፕሬተሮች፣ ቲኬተሮች፣ የቁጥጥር ባለሙያዎችና የመሳሰሉትን ለማሰልጠንም ዝግጅት እየተደረገ ነው፡፡

የባቡሩና የመኪኖች መንገድ አጠቃቀም
መኪናዎችና ባቡሩ በመስቀለኛ መንገዶች ላይ እንዴት ይተላለፋሉ ብለን የጠየቅናቸው ኢንጂነር በሃይሉ፤ የባቡሩ መስመር አይነት በከፊል የተዘጋ የሚባለው ሲሆን ራሱን ችሎ ከመኪና መንገድ ጋር ሳይገናኝ የመጓዙን ያህል በሌላ በኩል ከመኪኖች ጋርም መንገድ የሚጋራባቸው ጥቂት ቦታዎች እንደሚኖሩ ይናገራሉ፡፡ ባቡሩ ከመኪኖች ጋር ሊገናኝ የሚችለው ወደ ኋላ በሚመለስበት ጊዜና በመስቀለኛ መንገድ ላይ ነው፡፡ ባቡሩ ከመኪናዎች ጋር በሚቆራረጥባቸው የተወሰኑ ቦታዎች አካባቢ ሲደርስ፣ ከርቀት የሲግናል ማመላከቻዎች በመጠቀም መኪኖች በቀይ መብራት እንዲቆሙ ይደረጋል፡፡ ባቡሩ በፍጥነት ሲያልፍ ወዲያው መኪኖቹ ይለቀቃሉ፡፡
የአፍሪካ ሃገራት ልምድ ምን ይመስላል?
በአፍሪካ ውስጥ የቀላል ባቡር አገልግሎት የተስፋፋ አይደለም ይላሉ - ኢንጂነሩ፡፡ ከ54 የአፍሪካ ሀገራት መካከል የከተማ ባቡር ተጠቃሚ የሆኑትና ለመሆን እየሰሩ ያሉት ኢትዮጵያን ጨምሮ ሰባት ሀገራት ብቻ ናቸው፡፡ እነሱም የሰሜን አፍሪካ ሀገራት እና ደቡብ አፍሪካ ናቸው፡፡ ከሰሜን አፍሪካ የካይሮ ሜትሮ ባቡር ተጠቃሽ ነው፡፡
በተመሳሳይ ኢትዮጵያ ልምድ የወሰደችበት የቱኒዚያ ቀላል ባቡር አገልግሎትም ተጠቃሽ ነው፡፡ በሌላ በኩል በአልጄሪያ፣ ሞሮኮ እንዲሁም በደቡብ አፍሪካ ጆሃንስበርግ፣ ፕሪቶሪያ እና ኬፕታውን የተለያየ አይነት የከተማ ባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት አለ፡፡ በግንባታ ላይ ካሉት ደግሞ በናይጄሪያ ሌጐስ እና አዲስ አበባ ላይ የተዘረጉት ፕሮጀክቶች ተጠቃሽ ሲሆኑ የአዲስ አበባው ከሰሃራ በታች ካሉ ሃገራት ቀዳሚው ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

የባቡር መስመር ግንባታው ሂደት
በመሬት ላይ የሚገነባውና በድልድይ የሚገነባው የባቡር መስመር በጥሩ ሂደት ላይ ሲሆኑ እንደሆነ የሚናገሩት ኢንጂነር በኃይሉ፤ ከሁሉም የላቀ ስራ የተከናወነው በመሬት ውስጥ በሚገነባው የባቡር መስመር ነው ይላሉ፡፡
በድልድይ የሚገነባው መስመር ከወሰን ማስከበር ጋር በተያያዘ አንዳንድ ችግሮች እንዳጋጠሙት ግን አልሸሸጉም፡፡ በተለይ ከመስቀል አደባባይ እስከ ለገሃር ባለው መስመር ባለቤቱ የማይታወቅ ምናልባትም ጣልያን ሳያሰራው አይቀርም ተብሎ የተገመተ የውሃ ማስወገጃ ቦይ በግንባታው ላይ ጫና ፈጥሯል፤ ሌላው አካባቢ ግን በጥሩ ሂደት ላይ ነው ብለዋል - ኢንጂነር በኃይሉ፡፡
21 ኪሎ ሜትር በሚሆነው የፕሮጀክቱ አካል ላይ ሁሉም አይነት የግንባታ ክንውኖች እየተተገበሩ ሲሆን፤ አብዛኛው የግንባታ ስራ በ2006 ዓ.ም ይጠናቀቃል፡፡
የሃዲድ ማንጠፍ ስራዎችም በዚያው አመት ይጠናቀቃሉ ተብሎም ይጠበቃል፡፡ የኤሌክትሪፊኬሽን ስራዎችም በብዛት ይሰራሉ፡፡
በ2007 ዓ.ም መጨረሻ ላይ የመጀመሪያው ምዕራፍ ሙሉ ለሙሉ ተጠናቆ ስራ ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የባቡር ፕሮጀክቱ በቻይናው የባቡር መንገድ ግንባታ ድርጅት የሚከናወን ሲሆን የፕሮጀክቱ ጠቅላላ ወጪ 475 ሚ.ዶላር ነው፡

 

 

(ሃርያ ላግድ ጐስያ ጐችድ ጌድዋ ካልዮጌ ዮሳመለቼስ)
ከዕለታት አንድ ቀን አያ አንበሳና ሰው ወዳጅ ሆኑ አሉ፡፡ “እዚህ ከምንቀመጥ ለምን በጫካ ውስጥ ዞር ዞር እያልን እግራችንን አናፍታታም” አለ ሰው፡፡
አንበሳም፤ “እኔ ጫካው ሰልችቶኛል፡፡ መንቀሳቀስ ከሆነ የፈለግከው ወደሚቀጥለው ከተማ እንሂድ”
ሰው፤ “መልካም፡፡ እየተዘዋወርን የከተማውን ሁኔታ እንይ”
በዚህ ተስማምተው መንገድ ጀመሩ፡፡
መንገድ ላይ ጨዋታ አንስተው ሲወያዩ የየራሳቸውን ዝርያ አንስተው ማውራት ጀመሩ፡፡
“እናንተ የሰው ልጆች’ኮ የእኛን የአንበሶችን ያህል ጥንካሬ የላችሁም፡፡ እኛ የዱር አራዊትን ሁሉ አስገብረን በእኛ ሥር እንዲሆኑ አድርገናል፡፡ እናንተ ግን እርስ በርሳችሁ እንኳን መስማማት አቅቷችሁ፤ ጦርነት፣ ዝርፊያና እልቂት ውስጥ ትገኛላችሁ” አለ አንበሳ፡፡
ሰውም፤ “አይደለም፡፡ እኛ የሰው ልጆች፤ የዓለምን ሥልጣኔ ለመምራት ሁልጊዜም ከላይ ታች ስንል፣ ያለውን ሃብት በጋራ ለመጠቀም፣ በእኩል ለመከፋፈል፣ ስንጣጣር ነው ግጭት የሚፈጠረው፡፡ ሌላው ቀርቶ አንተ የምትኖርበትን ጫካና ደን እንዳይጨፈጨፍ ባንታገል ኖሮ ይሄኔ መኖሪያ አጥተህ ነበር” ይለዋል፡፡
አንበሳም፤
“እሱ ለእኛ በማዘን ሳይሆን የራሳችሁን ህይወት ለማራዘም ስትሉ የምታደርጉት ነው፡፡ እኛ የተፈጥሮ ጥንካሬያችን ብቻ ያኖረናል”
ሰው፤ “በሽቦ በታጠረ መናፈሻ ውስጥ እንድትኖሩ የእንስሳት ማቆያም እኮ አዘጋጅተንላችኋል፡፡ አንበሳ፤ “እሱም ቢሆን እኛን ለቱሪስት እያሳያችሁ ገንዘብ የምትሰበስቡበት ነው፡፡ ለእኛ እሥር ቤት ነው”
በዚህ ማህል አንድ አደባባይ ጋ ይደርሳሉ፡፡ አደባባዩ መካከል ሐውልት አለ፡፡ ሐውልቱ አንድ ሰው አንድ አንበሳን ታግሎ ሲጥለው የሚታይበት ስዕል አለው፡፡
ይሄኔ ሰውዬው በአሸናፊነት ስሜት፤
“ተመልከት፤ የሰው ልጅ አንበሳን እንዴት እንደሚያሸንፈው!” አለው፡፡
አንበሳም፤ “ይሄ ያንተ አመለካከት ነው፡፡ ይህንን ሐውልት የሠራነው እኛ አንበሶች ብንሆን ኖሮ፣ አንበሳውን ከላይ፣ የሰውን ልጅ ከታች አድርገን እንቀርፀው ነበር!” አለው፡፡
***
ሁሉ ነገር ሁለት ወገን እንዳለው አንርሳ፡፡ ከማን አቅጣጫ ነው የምንመለከተው ነው፤ ጉዳዩ፡፡ ሁሉም እኔ ነኝ ጠንካራ ይበል እንጂ ጠንካራው በመካያው ይለያል፡፡ ዕውነተኛው፤ የማታ የማታ መለየቱ የታሪክ ሂደት ነው፡፡
“ዳገት ከላይ የሚያዩት ቁልቁለት፣ ቁልቁለት ከታች የሚያዩት ዳገት” እንዳለው ነው ገጣሚው፡፡
መቼ ቁልቁለቱ ዳገት እንደሚሆንብን ካላስተዋልን “ያሰፈሰፈው መዓት” ይጠብቀናል (The impending catastrophe እንዲሉ)፤
ሐውልቱን፤ ጊዜ የሰጠው ይሠራዋል፡፡ አንድ የቀድሞ የደርግ ጄኔራል በሰጡት ኢንተርቪው፤ “ስለደርግ በሚያወራ የቴሌቪዥን ፕሮግራም በቀዳሚነት የሚታዩት እርሶ ነዎት - ውስኪ ሲጠጡ፡፡ ምን ይሰማዎታል?” ቢባሉ፤ “ይሄ ምንም አይገርምም፡፡ እኛ በጊዜያችን ውስኪ ጠጣን! እነሱም ይሄው በጊዜያቸው ውስኪ እየጠጡ ነው” ብለው መልሰዋል፡፡ ጊዜ ፈራጅ ዳኛ ነው፡፡
ዛሬም የሀገራችን ቁልፍ ጉዳይ መቻቻል ነው፡፡ መቻቻል ብስለትንና ዕውቀትን አጣምሮ የያዘና ጊዜን በቅጡ ግንዛቤ ውስጥ የሚያስገባ ዕሳቤ ነው፡፡ መልካም ባሕል ያለው ህዝብ የታደለ ነው፡፡ የባህሉ ጥንካሬ ለመቻቻሉ ብርቱ አስተዋጽኦ ያደርጋል፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ እንደዚያ ነው፡፡ እኔ ብቻ ነኝ ጠንካራ የሚል አመለካከት ከመቻቻል ጋር ግንባር ለግንባር ይጋጫል፡፡ “እኔ ነኝ የበላይ” የሚል አስተሳሰብን ያመላክታልና፡፡ መካረርና ማክረር ከጽንፈኛና ከፅንፈኝነት ጐራ መክተቱ እውን ነው፡፡ መጭው ነገር አስቀድሞ ጥላውን ይጥላል፡፡ (Coming events cast their shadows) እንደሚሉት ፈረንጆች) (ለላመት የሚቆስል እግር ዘንድሮ ዝምብ ይወረዋል፤ እንዳለውም አበሻ)
የሩቁን ያላስተዋለ አለቃ፣ ኃላፊ ወይም መሪ፣ አስተውሎም ያላመዛዘነ፤ አመዛዝኖም በጊዜ እርምጃ ያልወሰደ ከሆነ፤ በአደጋው ውስብስብ መረብ ውስጥ ገብቶ መተብተቡ አይቀሬ ነው፡፡ ብርቱ ጥንቃቄ ያሻል፡፡ ስለዲሞክራሲ መጠንቀቅ ዋና ጉዳይ ነው፡፡ ስለሃይማኖት መጠንቀቅ የበለጠ ዋና ጉዳይ ነው፡፡ ሰው እንደቤቱ እንጂ እንደጐረቤት አይኖርምና ሁሉም ወገን ሊያስብበት የሚገባ ጥልቅና ጥብቅ ጉዳይ ነው፡፡
እንደተጣደ ወተት መቼ ሊገነፍሉ እንደሚችሉ የማናውቃቸውን ነገሮች በዐይነ-ቁራኛ ማየት፤ ተገቢውን ማርከሻ ማወቅና መጠቀም ተገቢ ነው፡፡ እንደ ሙስና፣ ኢፍትሐዊነት፣ የዕምነት - ሽፋን ሂደቶች… ወዘተ ጉዳዮች በትኩረት መጤን ያለባቸው ናቸው፡፡
ሬዲዮው ያወራል በተግባር ምንም የለም፡፡ ቴሌቪዥኑ ያሳያል በተግባር የለም፡፡ ጋዜጣ ይፅፋል በግብር ምንም የለም፡፡
The rottener the time the easier it is to get promoted ይላል ሔልሙት ክሪስት የተባለ ፀሐፊ፡፡ (ጊዜው ወይም ዘመኑ እየተበሳበሰ ሲሄድ የሥራ ዕድገትና ሹመት በሽበሽ ይሆናል እንደማለት ነው፡፡) የተሾምንበት፣ የአደግንበት ሥራ ተግባርን ግድ እንደሚል ደጋግመን እናስብ፡፡ ምን አልሠራንም የምንለውን ያህል የሠራነው ተገቢ ነወይ? ብለንም ለመጠየቅ እንትጋ!
የትውልድ ዝቅጠትና መበስበስ (decadence) የፖለቲካውና የሶሺዮ ኢኮኖሚው ድቀት የሚያመጡት ክስተት ነው፡፡ እጅግ በከፋ ገፁ ሲታይ ከሀገራችን ከውይይት ይልቅ ግጭት፣ ከሰላም ይልቅ ጦርነት ይዘወተራል፡፡ በእንዲህ ያለው ዘመን አፍ ይበዛል፡፡ አዕምሮ ይደርቃል፡፡ አንድ ደራሲ እንደሚለው verbal diahria and mental constipation በይፋ ይታያል፡፡ (የአፍ - ተቅማጥና የአዕምሮ - ድርቀት ይንሰራፋል እንደማለት ነው፡፡ መለፍለፋ፣ መለፍለፋ፣ መለፍለፋ ብቻ፡፡ ሐሳብ የለም፡፡ ዕውቀት የለም፡፡ ጥበብ (wisdom) የለም፡፡ ተግባር - አልባ ልፍለፋ! ለዚህ ነው ከልኩ በላይ የተመኘነው ለውጥ በቀላሉ የማይመጣው፡፡ የአፍ መብዛት፣ የስብሰባ መብዛት… የግምገማ መብዛት ብቻውን ፍሬ እንደማያፈራ ደጋግመን ተናግረናል፡፡ የሚሰማ አለመኖሩ ነው ምላሹ፡፡
“የምንለውን ብለናል የምናደርገውን እንጀምር!” አሉ አሉ የቀድሞው መሪ፡፡ ስላልን የሠራን እንዳይመስለን ነው ነገሩ፡፡
“አህያ እየነዱ፣ ቅል እየሳቡ፣ ከኋላ ሲከተሉ፤ ወተት ያለቡ ይመስላል” የሚለው የወላይታ ተረት ሁኔታውን የበለጠ ይገልፀዋል፡፡

Saturday, 10 August 2013 10:33

ለካ ሞት ግጥም አይችልም!!

እንደመግቢያ
ክፍት የሥራ ቦታ
ግጥም ፅፌ ፅፌ፣
አላነብም ብሎ ሰዉ ቢያስቸግረኝ
“ክፍት የሥራ ቦታ”፣ የሚል ከባድ ርዕስ-ያለው ግጥም ፃፍኩኝ!
ማ ጮክ በል አለኝ?... ተሻማ ህዝብ ሁሉ፣ግጥሜን ገዛልኝ!
በየቤቱ ሄዶ-ተስገብግቦ ጠግቦ፣ ዋለበት ቢመቸው-
ሦስቴ አራቴ፣ አምስቴ፤ ደጋግሞ አነበበው-
ግጥሙ እንዲህ አለቀ፡-
“ውድ አንባቢዬ ሆይ በቢሮ፣ በቤትህ፣ በፍራሽ ላይ ያለህ
መንግስት ያላየውን፣ ውለታ ዋልኩልህ፡፡
ምሁር ያልተካነው፣ ትምህርት አስተማርኩህ፡፡
ትግል ያልፈታውን፣ ቅን መላ ሰጠሁህ፡፡
ይህን በማንበብህ፣ የሥራ-አጥ ቁጥር፣ በጦቢያ ቀነሰ
ቢያንስ የዛሬውን ቀን፣ ስራ በማግኘትህ የልብህ ደረሰ!!
ግጥሜም ስራ አገኘ የአንጀት አደረሰ
እኔም ስራ አገኘሁ ምኞቴ ታደሰ!!
የዕድሜ ሙሉ መክሊት፣ ለዛ ነው አስቤዛ
እንዲህ ያለው ስራ በዋዛ አይገዛ!!

ውለሃል በል አንጋ
ፌዝ አይደለም ቅኔው፣የስራ ፍለጋ
ስራ ስትፈልግ ብቅ በል እኔጋ!...
ልምድ ይኑር አይኑርህ
አበባም ሁን ቀጋ
ወለላም ሁን ፉንጋ
ደማም ሁን ጠሟጋ፤
ወጣት ሆይ ነብር ጣት! ልክ እንደተመረቅክ፣ ብቅ በል ግጥም ጋ!!
ማስታወቂያ መስሎት ይህን ግጥሜን ሰምቶ
“ስራ እፈልጋለሁ” ብሎ ተሟሙቶ
ሞት መምጣቱን ሰማሁ እሱም ስራ ሽቶ!....
(ለዓለም ባንክ እና ለስራ - አጡ ወጣት እንዲሁም ለፀጋዬ ገ/መድህን
ሐምሌ 2005ዓ.ም
ለካ ሞት ግጥም አይችልም
ሰሞኑን፣
ሞትን መንገድ ላይ አየሁት፡፡
አለባበሱ ገረመኝ፡፡
ዥጉርጉር ቲ-ሸርት አድርጓል
ከታች ራንግለር ለብሷል!
አሃ?!
እሱም ፋሽን ይከተላል? ፍንዳታ መሆን ያምረዋል?
ያው እቲ-ሸርቱም ላይኮ፣ ከፊቱም ገፅ፣ ከኋላውም፤
መፈክር መሳይ ተፅፏል፡፡
ከፊት ለፊቱ በኩል፣ long live death ይላል
“ሞት ለዘላለም ይኑር”
ከጀርባው follow me ይላል “ተከተይኝ” ስለፍቅር!
ወይ ጉድ፤ ይሄስ ሞት ይገርማል!
ይሄ ጅል የጅል ቆንሲል
እሱም ህይወት ይፈልጋል?
ፍቅረኛ ማግኘት ያምረዋል?
ሞት፤የብርሃን ባላንጣ፣ ፀሀይ ይፈራል መሰል
ጥቁር ዣንጥላ ዘርግቷል፡፡
በእጁ ደሞ እንደወጉ፣ ደብተርና እርሳስ ይዟል!
እኔ፤ ገጣሚው ልቅሶ ቤት፤ ልቤን ላነባ ስገባ
ሞትም ተከትሎኝ ገባ፡፡
እኔ ወዲህ ማዶ ቆምኩኝ
እሱ ወዲያ ማዶ ቆመ
ከማህል ገጣሚው አለ
የፊደል አርበኛ አደለ? አስከሬኑ ጃኖ ለብሷል
ገጣሚ ማለት ፈሣሽ፣ ስደተኛ ወንዝ አደለ?-
ወንዝ አለት እንደሚንተራስ፣ ብረት ሳጥን ተንተርሷል፡፡
ሞትን ከገጣሚው ማዶ፣ በስሱ አሻግሬ እያየሁ፣
“ለምን መጣህ?” ብዬ ብለው
ሞት ፈጣጤ አፍ-አውጥቶ
“ግጥም ልማር!” አለኝ ኮርቶ፡፡
ይሄኔ ገጣሚው ነቃ!
አስክሬኑ ተግ አለና
ብድግ አለ ከተኛበት!
ሞትን በደም ዐይኑ አየና
“ሀጠራው!” አለ
‘ሞት ለዘላለም ይኑር!’
የሚል ሸቃባ መፈክር
እርኩስ ደረትህ ላይ ፅፈህ
ግጥም መማር ታስባለህ?
ግጥም የህያው ልሣን ነው፣ ለሞት አንደበት አይሆንም፡፡
የስንኝ ጠበል እሚፈልቅ፣ በድን አለት ውስጥ አደለም፡፡
ግጥም ከነብስ ቃል እንጂ፣ ከሥጋ ትንፋሽ አይነጥብም፡፡
አንዳች ህይወት ውስጥህ ሳይኖር፣ ፊደል በመቁጠር አትገጥምም!!
አንተ ግንዝ ነህ ግዑዝ!
ጥላ የነብስ ባላንጣ
ዛሬ ደግሞ ብለህ ብለህ፣ ግጥም ልትማር ትመጣ?
ሀጠራው! ዐይን - አውጣ! ውጣ!”
ይህን ሰምቶ መልስ ሲያጣ
ሞት የሚባለው ፈጣጣ
ጭራውን ሸጉቦ ወጣ፡፡

ወይ ጉድ!
ስንቴ በኛ ቂም አርግዞ
ስንቱን ባለቅኔ ወስዶ፣ ስንቱን ቅኔ አግዞ አግዞ፤
“ግጥም ልማር መጣሁ” ይበል? ይሄ ሞት እሚባል ፉዞ
ያውም ከማይጨበጠው፣ ከእሳት አበባው ወዳጄ
ከንጋት ግጥም አዋጄ
ከሞት - ገዳዩ ቀኝ እጄ?
ግን፤
ምን ደስ አለህ አትሉኝም?
ለካ ሞት ግጥም አይችልም
ለካ ሞት ቅኔ አይገባውም!!
የካቲት 27/1998
(ለወዳጄ ለፀጋዬ ገ/መድህን እና ለጥበብ ለቀስተኞች)
/የጋሽ ፀጋዬ አስከሬን ከአሜሪካ መጥቶ፤ ቤቱ ሄጄ በተሰማኝ ስሜት መነሻነት የተፃፈ/ ብሔራዊ ቴያትር በፖለቲካ የግጥም ምሽት ላይ በነሐሴ ልደታ የተነበበ/

የመንግስት ስልጣን ገደብ ቢኖረው ኖሮ ሚኒስትር ዲኤታው ፍ/ቤት ይቆሙ ነበር - ኢ/ር ይልቃል ጌትነት፤ የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ናፍቆት ዮሴፍ “ሰማያዊ ፓርቲ፣ ግንቦት ሰባት እና አክራሪዎች ጋብቻ ፈጽመዋል” በሚል የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ መናገራቸውን የተቃወሙት የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት፤ “የፀረ ሽብር አዋጁ ካልተቀየረ ማንም አይምርም፣ የመንግስት ስልጣን ገደብ ቢኖረው ኖሮ ሚኒስትር ዴኤታው ፍ/ቤት መቆም ነበረባቸው” በማለት ምላሽ ሰጡ፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ በህዝብ ስም የተቋቋመ ስለሆነ የመንግስት ድክመቶችንና ክፍተቶችን እንዲያስተካክል መታገል ስራው ነው ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ መንግስት የህዝብን ጥያቄ ከመመለስ ይልቅ መፈረጅ ይቀናዋል፤ ይህ ግን ከትግላችን አያግደንም” ብለዋል፡፡

“ከሁለት ወር በፊት የህዝብ ችግሮችና ጥያቄዎች ናቸው ብለን በሰላማዊ ሰልፍ ያሰማናቸው ጥያቄዎች አልተመለሱም” ያሉት ኢ/ር ይልቃል፤ ነሐሴ 26 ቀን 2005 ዓ.ም ሁለተኛውን ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ ዝግጅት እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡ “ኢትዮጵያ ከአገዛዝ ወደ ዴሞክራሲ ገና አልገባችም፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ገና የስልጣን ባለቤት አልሆነም” ያሉት ኢንጂነሩ፤ እነዚህ ነገሮች እውን እንዲሆኑ በምርጫ ቦርድ ህጋዊ እውቅና አግኝቶ በሰላማዊ መንገድ የሚታገልን ፓርቲ ከአሸባሪዎች ጋር ጋብቻ ፈጽሟል በማለት መወንጀል የአገዛዝ ባህሪ ነው ሲሉ ተችተዋል፡፡ አሸባሪ የሚለው ቃል ትርጉሙን ስቷል የሚሉት ኢ/ር ዘለቀ፤ የፀረ ሽብር አዋጁ እስካልተቀየረ ድረስም ማንንም ከመፈረጅ የሚያግድ ነገር የለውም ብለዋል።

ከደቡብ ኮሪያው ግዙፍ የኤሌክትሮኒክስ ኩባንያ ሳምሰንግ የመጡ 100 አባላት ያሉት የበጐ ፈቃደኞች ቡድን፣ በቢሾፍቱ የህክምና ስልጠናዎችን በመስጠትና አስፈላጊ ቁሳቁሶችን በመለገስ ለአምስት ቀናት አገልግሎት እንደሰጡ ተገለፀ፡፡ ከሐምሌ 29 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ነሐሴ 3 ቀን 2005 ዓ.ም በተካሄደው የበጐ ፈቃድ አገልግሎት፣ ለቢሾፍቱና አካባቢዋ ነዋሪዎች የተለያዩ ህክምናዎችና የመድሀኒት አቅርቦት ተሰጥቷል፡፡ በርካታ ቁጥር ያላቸው ሕሙማን ወደ ኮሪያውያኑ በጎፈቃደኞች በመምጣት፣ የህክምና አገልግሎት ያገኙ ሲሆን ህክምናው ሙሉ ምርመራንና የመድሀኒት አቅርቦትን ያጠቃልላል፡፡
የበጐ ፈቃደኞች ቡድኑ ከህክምና ባለሙያዎች በተጨማሪ በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሙያ ላይ የተሰማሩ አባላትንም ያካተተ ሲሆን በቢሾፍቱ ቴክኒክና ሙያ ት/ቤት ግቢ ውስጥ ለአምስት ቀናት አገልግሎት ሲሰጡ መቆየታቸውም ታውቋል፡፡