Administrator

Administrator

ምርጫ ቦርድ በህገወጦች ላይ የከፋ እርምጃ እወስዳለሁ ብሏል
ሞባይል ስልክ ይዞ መግባት አይፈቀድም

ነገ በሚካሄደው 5ኛው አገር አቀፍ ምርጫ ላይ በየምርጫ ጣቢያዎቹ ጥብቅ ፍተሻና ጥበቃ እንደሚደረግ የጠቆመው ምርጫ ቦርድ፤ ከህግና ሥርዓት ውጪ ሆነው በተገኙ ወገኖች ላይ ጥብቅ እርምጃ እንደሚወሰድ አስታወቀ፡፡ መራጮች ወደ ምርጫ ጣቢያዎች በሚሄዱበት ወቅት ከምርጫ ካርዳቸውና ከመታወቂያ ወረቀታቸው ሌላ ምንም አይነት ነገሮችን ይዘው መግባት እንደማይፈቀድላቸውም ተገልጿል፡፡
የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መርጋ በቃና ከትናንት በስቲያ በሒልተን ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት፤ ምርጫው ሠላማዊ በሆነ መንገድ እንዲካሄድ ለማድረግ የሚያስችል ቅድመ - ዝግጅት ተጠናቋል፡፡ መራጮች ወደ ምርጫ ጣቢያ ሲሄዱ ሞባይል ስልካቸውንም ሆነ ሌላ ምንም ዓይነት መሣሪያዎችን ይዘው መግባት አይፈቀድላቸውም፡፡
የምርጫው በሰላማዊ መንገድ መጠናቀቅ የቦርዱ ኃላፊነት መሆኑን ያስገነዘቡት ፕሮፌሰር መርጋ፤ ይህንን ሁኔታ ለማስጠበቅም ሠላማዊ የምርጫ ሂደትን ለማደፍረስ በሚንቀሳቀሱ ወገኖች ላይ ቦርዱ የሚወስደው እርምጃ የከፋ ይሆናል ብለዋል፡፡ ለዚህ ደግሞ በቂ ዝግጅት ተደርጓል ሲሉ አስጠንቅቀዋል፡፡

አሁን የወጣቱ ልብና አዕምሮ ከአገር ውጭ ነው
ከፍተኛው የስደት መንስኤ የተሻለ ህይወት ፍለጋ ነው (ILO)
“በአገር ቤት ሰርቶ መለወጥ ይቻላል የሚለው ዲስኩር ለውጥ አያመጣም”
    አሊ ሃሰን፤ በቅርቡ በሜዲትራኒያን ባህር ህይወታቸውን ያጡት 8 የመርካቶ አባኮራን ሠፈር ልጆች አብሮ አደግ ነው፡፡ መጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ.ም “በሰላም ያግባችሁ” ብሎ የሸኛቸው አብሮ አደጐቹ ድንገት የሞታቸውን መርዶ ሲሰማ ክፉኛ ከመደንገጡ የተነሳ ማመን አቅቶት እንደነበር ይናገራል፡፡ “ቤተሰቦቻቸው በድህነት ያሳደጓቸው አብሮ አደጐቼ፣ ያልፍልናል ብለው ነው ህይወታቸው ያለፈው” የሚለው የ25 አመቱ አሊ፤ እነሱ ከወራት በፊት ወደ ሊቢያ ለመሻገር የሱዳን ቪዛ ሲሰጣቸው በቂ ገንዘብ በእጁ ላይ ባለመኖሩ ተነጥሏቸው እንደቀረና ገንዘብ ሲያገኝ እንደሚቀላቀላቸው ቃል ገብቶላቸው መለያየታቸውን ያስታውሳል፡፡ አሁን አሊ ወደ ሱዳን የሚያስገባውን የ2 ወር የቱሪስት ቪዛ ለማግኘት እየተሯሯጠ ሲሆን በቅርቡ ተጓዥ ነኝ ብሏል - ለአዲስ አድማስ፡፡ “ይህን ሁሉ ሞትና አሰቃቂ ነገር እየሠማህ እንዴት ትሄዳለህ?” በሚል ለቀረበለት
ጥያቄ ሲመልስ፤ “እነሱ እድላቸውን ሞክረው አልተሳካላቸውም፤ እኔም እድሌን ልሞክር” ነው ያለው፡፡ በሃገር ቤት ሠርቶ መለወጥ ይቻላል፤ አሹቅ በልተን በእናቶቻችን ጉያ ውስጥ መኖር ምናምን  የሚባለው ለኔ ትርጉም የለውም” የሚለው አሊ፤ እዚህ ሀገር ተቀምጬ እስከ መቼ ከእጅ ወደ አፍ የሆነ ኑሮ እመራለሁ ሲልም”  ይጠይቃል፡፡ ከሊስትሮ ጀምሮ አነስተኛ ሥራዎችን መስራቱን የሚናገረው ወጣቱ፤ ከ6 አመት በላይ የተለያዩ ተባራሪ የንግድ ስራዎችን ቢሰራም ከቤተሰብ ጥገኝነት መላቀቅ እንዳቃተው ይናገራል፡፡ ከእናቱና
ከሁለት እህቶቹ ጋር እንደሚኖር የጠቆመው አሊ፤ ከ3 አመት በፊት አባቱ መሞታቸውን ተከትሎ እህቶቹን የማስተማርና ወላጅ እናቱን የመጦር ሃላፊነት  እንደወደቀበት ይናገራል፡፡ ቤተሰቤ ፆም እንዳያድር ከጠዋቱ 12 ሰአት ጀምሮ እስከ ምሽት 2 ሰዓትና 3 ሰዓት ድረስ የተለያዩ ተባራሪ ስራዎችን ስሰራ ብውልም በቀን ከ60 እና 70 ብር በላይ ገቢ አላገኝም ይላል - ወጣቱ በምሬት። “በ70 ብር ምን ልታደርግበት ነው? ቁርስና ራትን እንተወውና ምሣ እንኳ ልብላ ቢባል ከ20 ብር በታች የሚሸጥ ምግብ የለም” የሚለው ወጣቱ፤ በቀን የሚያገኛትን 60 እና 70 ብር እንደምንም አብቃቅቶ ቤተሰቡን ከረሃብ እንደሚታደግ ነው የገለፀው፡፡ ግን በዚህ ሁኔታ እስከ መቼ እቀጥላለሁ በማለት ይጠይቃል፡፡ እናም ቀድሞ በጣሊያን አድርጐ እንግሊዝ ሃገር የገባ አብሮ አደጉ አሁን እስከ ሱዳን ሊያደርሰው የሚችል ገንዘብ እንደላከለትና በዚያም አስፈላጊውን የጉዞ ዝግጅት በማድረግ ላይ እንደሚገኝ ተናግሯል፡፡ ባለፈው ሳምንት የ7ቱን አብሮ አደግ ጓደኞቻቸውን ሞት የተረዱት የአባኮራን ሰፈር ወጣቶች፤ ክፉኛ አዝነው የነበረ ቢሆንም አብዛኞቹ ግን ከአገር የመውጣት ከፍተኛ ጉጉት እንዳላቸው ገልፀውልናል፡፡ “እዚህ ሃገር 24 ሰዓት ቢሠራ ጠብ የሚል ነገር የለም” የሚሉት ወጣቶቹ፤ ከሃገር ከተወጣ ግን በተጨባጭ መለወጥ እንደሚቻል ከዚህ ቀደም የሄዱ ጓደኞቻቸውን በምሳሌነት እየጠቀሱ ያስረዳሉ፡፡ በሳሪስ አቦ አካባቢ በሊስትሮ ስራ የተሠማራው ጋዲሣ፤ ከትውልድ ሀገሩ አምቦ ወደ አዲስ አበባ የመጣው በመዲናይቱ ሰርቶ ለመለወጥ የሚል ዓላማ አንግቦ ሳይሆን ፓስፖርት ለማውጣት ነው፡፡ ፓስፖርቱን ከ4 ወራት በፊት ማውጣቱን የሚናገረው ወጣቱ፤ አሁን ደግሞ የሱዳን ቪዛ ለማግኘት
እየጣረ መሆኑን ይገልፃል፡፡ “በአይኤስ አሸባሪ ቡድን ስለታረዱትም ሆነ በሜዲትራኒያን ባህር ስለሰመጡት ሰዎች በሚገባ ሰምቻለሁ፤ መስቀል አደባባይ አይኤስን ለማውገዝ በተጠራው ሠልፍ ላይም ተሳትፌያለሁ፤ ግን ወደ አውሮፓ በየትኛውም መንገድ የመሄድ ሃሳቤን አልሰረዝኩም። ምክንያቱም እዚህ ጠብ የሚል ነገር የለም፤ ጓደኞቼ የደረሱበት ደረጃ መድረስ እፈልጋለሁ” ሲል ዓላማውን ገልጿል፡፡ ከቴክኒክና ሙያ በአውቶ ኤሌክትሪሲቲ በሠርተፍኬት መመረቁን የሚናገረው ጋዲሳ፤ እንግሊዝ ወይም ፈረንሳይ ቢገባ በተማረው ሙያ ስራ ሊያገኝ እንደሚችል ተስፋ ያደርጋል፡፡ ከሁለት አመት በፊት በጣሊያን አድርገው እንግሊዝ የገቡ ሁለት አብሮ አደጐቹ በተማሩበት የመካኒክ ዘርፍ በጋራዥ ውስጥ ተቀጥረው እየሠሩ መሆኑን እንደነገሩት የጠቀሰው ወጣቱ፤ ጓደኞቹ በሁለት አመት ጊዜ ውስጥም ለቤተሰቦቻቸው ገንዘብ መላክ እንደጀመሩ ይናገራል፡፡ የተወሰነ ለጉዞው ጉዳይ ማስፈፀሚያ የሚሆን ገንዘብም ለእርሱ እንደላኩለት ገልጿል፡፡ እናትና አባቱ ከሞቱ በኋላ ከሶስት ወንድሞቹ ጋር የተካፈላትን ውርስ ሸጦ ለጉዞው የሚያስፈልገውን ገንዘብ ለማሟላት ማሰቡንም ይናገራል፡፡ በጉዞህ ላይ አደጋ ቢያጋጥምህስ? በሚል ሲጠየቅ፤ “እሱ የእድል ጉዳይ ነው፤ እድሌን እሞክራለሁ” ባይ ነው፡፡ በሌላ በኩል በ2006 ዓ.ም ከሣኡዲ በተባረሩ ኢትዮጵያውያን ዙሪያ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን ቀርፆ የሚንቀሳቀሰው የክርስቲያን ተራድኦ በጎ አድራጎት ድርጅት (CCRDA) ተመላሾቹ ስላሉበት ሁኔታ የሚገመግም የጥናት ሰነድ ሰሞኑን ይፋ ያደረገ ሲሆን ቀላል የማይባል ቁጥር ያላቸው የሣውዲ ተመላሾች ተመልሰው ከሃገር መሰደዳቸው ተጠቁሟል፡፡ በፕሮግራሙ ላይ ተጋባዥ ከነበሩ ጥቂት ተመላሾች መካከልም ሁለት ወጣቶች አሁን ያሉበትን ሁኔታ ለተሰብሳቢው ገልፀው ነበር፡፡ ሣውዲ አረቢያ በሰው ቤት ለሁለት አመት ተቀጥራ ትሠራ እንደነበር የገለፀችው በ20ዎቹ መጀመሪያ ላይ የምትገኘው ዘይነብ፤ ለሁለት አመት የሠራችበት ደሞዟን ተከልክላና ተባራ ጐዳና ወድቃ የነበረ ባዶ እጇን ወደ ሀገሯ እንደተመለሰችም ትናገራለች፡፡ በወር 700 ሪያል እንደሚከፈላት ተዋውላ ትሠራ እንደነበር የገለፀችው ዘይነብ፤ ሣውዲ ለሁለት አመታት የደከመችበት ወደ 16ሺህ ሪያል ገደማ ሣይከፈላት ባዶ እጇን ከተመለሰች በኋላ አንድ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት አስጠግቷት ለአንድ አመት እንደተንከባከባትና ከአንድ አመት በኋላ በምግብ ስራ ሙያ አሠልጥኗት ከ8 ሺህ ብር በላይ አውጥቶ የማብሰያ ማሽን ገዝቶ በመስጠት “በዚህ ስሪና ራስሽን ለውጪ” እንዳላት ተናግራለች፡፡ ይሁን እንጂ ዘይነብ ማሽኑን ታቅፎ ከመቀመጥ ውጪ ሥራ ልትሠራበትና ህይወቷን ልታሻሽልበት አልቻለችም፡፡ “መንግስት የመስሪያ ቦታ ሊሠጠኝ ፍቃደኛ ባለመሆኑና የንግድ መነሻ የሚሆን ገንዘብም ማግኘት ባለመቻሌ ዝም ብዬ ተቀምጬአለሁ” ብላለች፡፡ “በወጣትነቴ የሰው ጥገኛ ሆኜ መኖሬ ያሳስበኛል” ስትል የምታማርረው ዘይነብ፤ በሳውዲ ብዙ ግፍና መከራ የደረሰባት ቢሆንም አሁንም እድሉን ብታገኝ ወደዚያው አሊያም ወደ ሌላ ሀገር ከመሄድ ወደ ኋላ እንደማትል ገልፃለች፡፡ ሀገር ቤት ባለው ሁኔታ ተስፋ መቁረጧንም ወጣቷ በምሬት አስረድታለች፡፡
ሣውዲ እያለች ልጆቿን ጥሩ ትምህርት ቤት ታስተምር፣ ቤተሰቦቿንም በሚገባ ትረዳ እንደነበር ያወሳችው ሌላኛው ወጣት በበኩሏ፤ በአሁን ሰአት ከልጆቿ ጋር የቤተሰቦቿ ጥገኞች ለመሆን እንደተገደዱ ትገልፃለች፡፡
“በቴሌቪዥን ስጠየቅ በሃገር ቤት ሠርቶ መለወጥ ይቻላል ብዬ ነበር” ያለችው ወጣቷ፤ አሁን ግን ይሄን የማለት ድፍረት የለኝም ብላለች፡፡ መንግስት አደራጅቶና ብድር አመቻችቶ መለስተኛ የንግድ ስራ ከጓደኞቿ ጋር መጀመሯን እንዲሁም እዳቸውንም መክፈል መጀመራቸውን የጠቆመችው ወጣቷ፤ እዳቸውን እንኳ ሳይጨርሱ የ5ሺህ ብር ግብር እዳ አለባችሁ እንደተባሉ ተናግራለች፡፡ “በዚህ ሁኔታ እንዴት ነው ተመላሾች ሊቋቋሙና በሀገራቸው ሠርተው ሊለወጡ የሚችሉት?” ስትልም ትጠይቃለች፡፡በቤተሰቦቿ እጅ ላይ ተመልሣ መውደቋ ክፉኛ እንደሚያሳስባት የገለፀችው ወጣቷ፤ የቤተሰቦቿንም ሆነ የልጆቿን ህይወት ቀድሞ ወደነበረበት ለመመለስ የግዴታ ወደ ውጭ ወጥታ መስራት እንዳለባት ማመኗንና ለመሄድ አጋጣሚዎችን እየጠበቀች መሆኑን በምሬት ተናግራለች፡፡ በመድረኩ ላይ የታደሙት የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ተወካይ በበኩላቸው፤ መንግስት ስደቱን እያባባሱ ነው በሚላቸው ህገ ወጥ ደላሎች ላይ እርምጃ እየወሰደ መሆኑን እንዲሁም ዜጐች በሀገራቸው ሰርተው የሚለወጡበትን ሁኔታ ለማመቻቸት ከወትሮው በተለየ እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ከመንግስት ጐን ሌሎች ባለድርሻ አካላትና ህብረተሰቡ መሣተፍ እንዳለበትም ተወካዩ አሳስበዋል፡፡ መንግሥታዊ ባልሆነ ድርጅት ውስጥ የማህበረሰብ ጥናት (ሶሺዮሎጂ) ባለሙያ በመሆን የሚሰሩት ዶ/ር ተካልኝ አባተ በበኩላቸው፤ አሁን ከመንግስት እየቀረቡ ያሉት ምክንያቶችና የመፍትሔ ሃሳቦች በቂም፤ አሣማኝም አይደሉም ይላሉ፡፡ “በሃገር ቤት ሠርቶ መለወጥ ይቻላል የሚለው የቀን ተቀን ዲስኩር አሠልቺ ከመሆን ያለፈ የግንዛቤ ለውጥ አያመጣም፣ መንግስት የፖሊሲ አማራጮቹን በሚገባ ማየትና መገምገም ይገባዋል” ብለዋል ምሁሩ፡፡ የማህበረሰብ ጥናት ባለሙያዎችን ጨምሮ የተለያዩ ምሁራን በጉዳዩ ላይ ጥልቀት ያለው ጥናትና ምርምር እንዲያደርጉም መንግስት መጋበዝ
እንዳለበት ዶ/ሩ ይመክራሉ፡፡ አለማቀፉ የሰራተኞች ድርጅት (ILO) ከግንቦት እስከ ሐምሌ 2014 ወደ አገራቸው በተመለሱ ስደተኞች ላይ ያደረገው ጥናት ውጤት እንደሚያመለክተው፤ ለስደታቸው መንስኤ ከሆኑ ምክንያቶች ከፍተኛውን ደረጃ የሚይዘው የተሻለ ህይወትን ፍለጋ የሚደረገው ስደት ነው፡፡ በህገወጥ ደላሎች ጉትጐታ አማካኝነት የሚደረገው ስደት እጅግ አነስተኛ ቁጥር ያለው መሆኑን አመልክቷል፡፡ እንደ ILO ሪፖርት፤ ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ከስደት ተመላሾች ዳግም መሰደድ የሚፈልጉ ናቸው፡፡




Saturday, 16 May 2015 11:29

የፍቅር ጥግ

ትዳር የዕድሜ ጉዳይ ሳይሆን ትክክለኛውን ሰው የማግኘት ጉዳይ ነው፡፡
ሶፍያ ቡሽ
ሚስቴ የልቤ ጓደኛ ናት፤ ያለ እሷ መኖርን ላስበው አልችልም፡፡  
ማት ዳሞን
 ትዳር ግሩም ተቋም ነው፡፡ ግን ማነው በተቋም ውስጥ መኖር የሚሻው?
ግሮቶ ማርክስ
ሴት ባሏን ለመለወጥ የማትሞክርበት ብቸኛ ወቅት ቢኖር የጫጉላ ሽርሽር ነው፡፡
ኢቫን ኢሳር
ሴት ለምንድን ነው 10 ዓመት ባሏን ለመለወጥ ከለፋች በኋላ “ይሄ ያገባሁት ወንድ አይደለም” ብላ የምታማርረው?
ባርባራ ስትሪላንድ
የትዳር ችግሩ በእያንዳንዱ ምሽት ፍቅር ከሰሩ በኋላ መፍረሱ ነው፡፡ እናም በእያንዳንዱ ጥዋት ከቁርስ በፊት እንደገና መገንባት አለበት፡፡
ጋብሬል ግራሽያ ማርኪውዝ
ትዳር ገነትም ገሃነምም አይደለም፤ የንስሃ ቦታ ነው፡፡
አብርሃም ሊንከን  
ደስተኛ ያልሆነ ትዳርን የሚፈጥረው የፍቅር እጦት ሳይሆነ የጓደኝነት (ወዳጅነት) እጦት ነው፡፡
ፍሬድሪክ ኒቼ
ጥሩ ባል ጥሩ ሚስትን ይፈጥራል፡፡
ጆን ፍሎሪዮ
ፍቅረኛህ ከጋብቻ በኋላ እንዴት እንደምትይዝህ ለማወቅ ከፈለግህ ከትንሽ ወንድሟ ጋር ስታወራ አዳምጣት፡፡
ሳም ሊቨንሰን
የመጀመሪያውን ለፍቅር ብለህ ታገባለህ፡፡ ሁለተኛውን ለገንዘብ ብለህ፣ ሶስተኛውን ለጓደኝነት ስትል ታገባለህ፡፡
ጃኪ ኬኔዲ

በአገሪቱ በተቀሰቀሰው ግጭት ከ20 በላይ ሰዎች ሞተዋል
      አገር ጥለው የተሰደዱ ዜጎች ከ500 ሺህ በላይ ደርሰዋል

    የቀድሞው የብሩንዲ የደህንነት ቢሮ ሃላፊ ሜጀር ጄኔራል ጎዲፍሮይድ ኒዮምባሬህ ባለፈው ረቡዕ በአገሪቱ መዲና ቡጁምቡራ ከሚገኝ የጦር ካምፕ በሬዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት፣ የፕሬዚደንት ኑኩሩንዚዛ አገዛዝ ማክተሙንና አገሪቱን የመምራቱን ሃላፊነት የሚረከብ ጊዜያዊ ብሄራዊ ኮሚቴ መቋቋሙን ያስታወቁ ሲሆን አገሪቱ በከፍተኛ ውጥረት ውስጥ ትገኛለች፡፡
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ከሌሎች አገራት መንግስታት ጋር በጉዳዩ ዙሪያ ለመምከር ወደ ታንዛኒያ መሄዳቸውን ተከትሎ፣ ጄኔራሉ በአገሪቱ መፈንቅለ መንግስት መካሄዱን ማስታወቃቸውንና በሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በቡጁምቡራ አደባባይ በመውጣት ደስታቸውን እንደገለጹ የዘገበው ቢቢሲ፤ አገዛዙን የሚቃወሙ ወታደሮችም በሁለት የጦር ታንኮች ታግዘው ወደ መዲናዋ ማዕከላዊ ክፍል ማምራታቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ተቃውሞው የበለጠ ተጠናክሮ መቀጠሉንና ከትናንት በስቲያም በመንግስት ጦርና በተቃዋሚ ሃይሎች መካከል በቡጁምቡራ ግጭት እንደተከሰተ የጠቆመው ዘገባው፣ ስርዓቱ ይፍረስ የሚለውን የተቃዋሚዎች አቋም በመደገፍ ተቃውሞውን ከተቀላቀሉት የአገሪቱ መከላከያ ሚኒስትር ጋር በተደረገ ድርድር መፈንቅለ መንግስቱ መቆሙን አንድ የአገሪቱ ጦር መሪ ማስታወቃቸውንም ገልጧል፡፡
ፕሬዚዳንት ንኩሩንዚዛ፤ መፈንቅለ መንግስት እንደታወጀባቸው ሲያውቁ ከታንዛኒያ ወደ ብሩንዲ ቢመለሱም፣ ሜጀር ጄኔራል ጎዲፍሮይድ ኒዮምባሬህ አውሮፕላን ማረፊያውና የአገሪቱ ድንበሮች እንዲዘጉ በማዘዛቸው፣ ፕሬዚዳንቱ ወደ አገራቸው መግባት እንዳልቻሉና ወደ ዳሬ ሰላም መመለሳቸውን ያስታወቀው የቢቢሲ ዘገባ፣ ፕሬዚዳንቱ በትዊተር ገጻቸው በኩል ከትናንት በስቲያ ባስተላለፉት መልዕክት የተቃውሞ እንቅስቃሴው በቁጥጥር ስር ውሏል፣ ህገመንግስታዊ ስርአቱም ከአፍራሽ ሃይሎች ተጠብቋል ብለዋል፡፡
የመንግስት ጦር የፕሬዚደንቱን ቤተ መንግስት፣ የብሄራዊ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ጣቢያውንና አውሮፕላን ማረፊያውን ጨምሮ በከተማዋ የሚገኙ ቁልፍ ቦታዎችን እንደተቆጣጠረ ቢያስታውቅም፣ የመፈንቅለ መንግስቱ መሪ ግን መዲናዋን ሙሉ በሙሉ በቁጥጥራችን ውስጥ አድርገናል ሲሉ አስተባብለዋል፡፡
የመፈንቅለ መንግስቱ ቃል አቀባይ ቬኖን ንዳባንዜ በበኩላቸው፤ “መንግስት ተቃውሞውን እንዲገቱ ያሰማራቸው ወታደሮችም ከጎናችን ቆመዋል፣ ድሉ የኛ ነው” ሲሉ ከትናንት በስቲያ ለአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ተናግረዋል፡፡
ከሲቪል ማህበረሰብ ቡድኖች፣ ከሃይማኖት መሪዎችና ከፖለቲከኞች ጋር በመሆን በአገሪቱ የሽግግር መንግስት መቋቋም የሚችልበትን ሁኔታ እያመቻቹ እንደሚገኙም ሜጀር ጄኔራል ጎዲፍሮይድ ኒዮምባሬህ ተናግረዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ኑኩሩንዚዛ ህገ መንግስቱ ከሚፈቅድላቸው ውጭ ያለ አግባብ ለሶስተኛ ዙር በፕሬዚዳንትነት ለመወዳደር መዘጋጀታቸውን የተቃወሙ በርካታ የአገሪቱ ዜጎች አደባባይ ወጥተው ተቃውሟቸውን ከማሰማት ባለፈ፣ አገዛዙን ከስልጣን ለማውረድ መነሳታቸውን የገለጹት ጄኔራሉ፤ ጊዜያዊ ኮሚቴው ብሄራዊ አንድነትን መልሶ በመፍጠርና ምርጫው በፍትሃዊና ሰላማዊ ሁኔታ መካሄድ የሚችልበትን ሁኔታ ለማመቻቸት  እንደሚሰራ አስታውቀዋል፡፡
ከሁለት ሳምንታት በላይ በዘለቀው ተቃውሞ ከ20 በላይ ዜጎች ለሞት መዳረጋቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ አገር ጥለው የተሰደዱ ብሩንዲያውያን ዜጎች ቁጥርም ከ500 ሺህ በላይ መድረሱን አመልክቷል፡፡

ዝንጀሮዎችም እንኳን ከዛፍ ላይ ይወድቃሉ፡፡
የጃፓናውያን አባባል
ሰባት ጊዜ ወድቀህ በስምንተኛው ተነስ፡፡
የጃፓናውያን አባባል
የበሰበሰ እንጨት አይቀረፅም፡፡
የቻይናውያን አባባል
አንዲት ውሸት ሺ እውነቶችን ታጠፋለች፡፡
የጋናውያን አባባል
አመድ መልሶ የሚበተነው ወደበተነው ሰው ፊት ነው፡፡
የናይጄሪያውያን አባባል
ለመብላት የቸኮለ አፉን ይቃጠላል፡፡
የሉሃያ አባባል
ሙቅ ውሃ የሆነ ጊዜ ላይ ቀዝቃዛ እንደነበር አይዘነጋም፡፡
የአይቮሪኮስት አባባል
የልብን ‹ወሬ› ከፈለግህ ፊትን ጠይቀው፡፡
የጊኒያን አባባል
በአፉ አጥንት የያዘ ውሻ መጮህ አይችልም፡፡
የዛምብያውያን አባባል
ሆድ ከፊት ለመሰለፍ አይፈራም፡፡
የናይጄሪያውያን አባባል
የመቃብርን ስቃይ የሚያውቀው የሞተ ሰው ብቻ ነው፡፡
የስዋሂሊ አባባል
አይጥ የቱንም ያህል ብትሰክር ድመት አልጋ ላይ መተኛት የለባትም፡፡
የካሜሩናውያን አባባል
ጨለማውን ከመራገም ሻማ ማብራት ይሻላል፡፡
የቻይናውያን አባባል
ዛፍ በፍሬው ይታወቃል፡፡
የዙሉ አባባል
ትንሽም ኮከብ ብትሆን ጨለማን ትሰብራለች፡፡
የፊንላንዳውያን አባባል
ዕድል ስትጎበኝህ ሁሉም ሰው የምትኖርበትን ያውቀዋል፡፡
የቻይናውያን አባባል
ጥሩ ምክር እንደሚመር መድኀኒት ነው፡፡
የቻይናውያን አባባል



 የኢራቅ መከላከያ ሚኒስትር አይሲስ በመባል የሚጠራው ጽንፈኛ አራጅ የሽብር ቡድን ምክትል መሪ የሆነው አቡአላ አልአፍሪ በህብረቱ ሀይሎች በተካሄደ የአየር ጥቃት ባለፈው ማክሰኞ መገደሉ ይፋ ተደርጓል፡፡  
በዩቲውብ የተለቀቀው አጭር የቪዲዮ ፊልም እንደሚያሳየው፤ አቡ አላ አልአፍሪ የተገደለው በኢራቅ የታል አፋር ከተማ በሚገኝ አንድ መስጊድ ውስጥ ነው፡፡ አብዱራህማን ሙስጠፋ አልቃዱሊ በሚል ተለዋጭ ስም የሚታወቀውና በ1957 ሞሱል ከተማ ውስጥ የተወለደው አቡ አላ አልአፍሪ የኢራቅ የአልቃኢዳ ቡድን ምክትል መሪና የሞሱል ከተማ ክንፍ ዋና አዛዥ በመሆን አገልግሏል፡፡
የፊዚክስ መምህር የነበረው አቡ አላ አልአፍሪ፤ የኢራቅ የአልቃኢዳ ምክትል መሪ በነበረበት ወቅት በኦሳማ ቢንላደን  ዘንድ ከፍ ያለ ሞገስ ማግኘት የቻለና ለአይሲስ ከፍተኛ መሪነት በዋናነነት የታጨ ሰው ነበር፡፡ የቱርክሜን ብሔረሰብ አባላት ከሆኑ የአይሲስ ከፍተኛ መሪዎች ግንባር ቀደም የሆነው አቡአላ አልአፍሪ የአይሲስ ዋነኛ መሪ መሆን ያልቻለውና የመሪነቱ ስልጣን ለአቡበከር አልባግዳዲ የተሰጠው አቡበከር አልባግዳዲ የዘር ሀረጉ ከነብዩ ሞሀመድ የዘር ሀረግ ስለሚመዘዝ ብቻ ነው፡፡
አቡአላ አልአፍሪ ከመገደሉ በፊት በተፈፀመበት የአየር ጥቃት ክፉኛ ቆስሎ አልጋ ላይ የዋለውን የአይሲስ መሪ አቡበከር አልባግዳዲን ተክቶ ቡድኑን ሲመራ ነበር ተብሏል፡፡
አሜሪካ በቁጥጥር ስር ለማዋል በጥብቅ ከምትፈልጋቸው ዋነኛ አሸባሪዎች ውስጥ አንዱ መሆኑን በመጥቀስ “ጠቁሞ ላስያዘው” የ7 ሚ. ዶላር ወሮታ እከፍላለሁ ስትል የነበረ ሲሆን የአቡአላ አልአፍሪን መገደልን ገና አምና የተቀበለችው አትመስልም፡፡ የዚህን ነብሰ በላ አሸባሪ መሞት ባይኔ በብረቱ አይቼ ካላረጋገጥኩ በቀር የሰውየው መገደል ዜና ከሆዴ አይገባም ብላለች፡፡

Saturday, 16 May 2015 11:06

የፀሐፍት ጥግ

ህክምና ህጋዊ ሚስቴ ናት፤ ስነፅሁፍ ውሽማዬ ናት፡፡ አንዳቸው ሲሰለቹኝ ከአንዳቸው ጋር ሌሊቱን አሳልፋለሁ፡፡
አንቶን ቼኮቭ
የሥነፅሁፍ ማሽቆልቆል የህዝብን ማሽቆልቆል ያመለክታል፡፡
ቮን ገተ
ግጥም የሥነ ፅሑፍ ዘውድ ነው፡፡
ሶመርሴት ሟም
ባህልን ለማጥፋት መፃሕፍትን ማቃጠል የለብህም፡፡ ሰዎች መፃሕፍት እንዳያነቡ ማድረግ ብቻ በቂ ነው፡፡
ሬይ ብራድበሪ
ህይወት ያለ ስነፅሁፍ ገሃነም ነው፡፡
ቻርለስ ቡከውስኪ
የምታነበው ሳይንስ ከሆነ አዳዲሶቹን ሥራዎች አንብብ፡፡ ሥነፅሑፍ ከሆነ ግን የጥንቶቹን አንብብ፡፡
ኢድዋርድ ጂ. ቡልዌር - ሊቶን
ሴቶች፤ ፍቅር ረዥም ልብወለድ እንዲሆን ይሻሉ፤ ወንዶች ደግሞ አጭር ልብወለድ፡፡
ዳፍኔ ዲ ማውሪየር
ቤተ መፃህፍት ውስጥ የሚጠፋ አንድ ሰዓት፣ በቤተ ሙከራ ውስጥ ከሚጠፋ አንድ ወር ጋ እኩል ነው፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
መፃሕፍት በሌሉበት መኖር አልችልም፡፡
ቶማስ ጄፈርሰን
መፃሕፍት በሁለት መደቦች ይከፈላሉ፡፡ የወቅቱ መፃህፍትና የምንጊዜም መጻህፍት በሚል፡፡
ጆን ሩስኪን
ንባብ ሙሉ ሰው፤ ጥሞና ጥልቅ ሰው፣ ንግግር ደግሞ ግልፅ ሰው ያደርጋሉ፡፡
ቤንጃሚን ፍራንክሊን
ማንበብ በራስ ጭንቅላት ከማሰብ ይልቅ በሰው ጭንቅላት ከማሰብ እኩል ነው፡፡
አርተር ስኮፊነር
በህይወት ውጣ ውረድ ውስጥ ብልሆች መፅናኛቸውን የሚያገኙት ከመፃሕፍት ነው፡፡
ቪክቶር ሁጎ
ሳላነብ ከምቀመጥ ይልቅ የጊዜ ሰሌዳ ወይም ካታሎግ ባነብ እመርጣለሁ፡፡
ሶመርሴት ሟም
መፃህፍትን ማንበብ ያለብህ እንደ መድኀኒት በትዕዛዝ እንጂ በማስታወቂያ አይደለም፡፡
ጆን ሩስኪን

በሀገሪቱ በጤናው መስክ የሚታየውን የመረጃ ክፍተት ለመሙላት፣ በዘርፉ ያለውን የእርስ በርስ ግንኙነት ለማጎልበትና ለጤና አገልግሎት ተጠቃሚዎች አመቺ የመረጃ ምንጭ እንዲሆን ታስቦ የተዘጋጀው “ኢትዮ ሄልዝ ዳይሬክተሪ” የተሰኘ የጤና አገልግሎት ማውጫ ከትናንት በስቲያ ተመረቀ፡፡
በዘርፉ በአይነቱ የመጀመሪያ የሆነው ይህ የጤና አገልግሎት ማውጫ፣ በይዘቱ ምሉዕ እና ከሁለት አመት በላይ በፈጀ የመረጃ ስብሰባ የተዘጋጀ ሲሆን መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ የጤና አገልግሎት ሰጪዎችን፣ የሆስፒታሎችን፣ የመድሃኒትና የሕክምና መገልገያ መሳሪያዎች አስመጪዎችን እና ሌሎች ባለድርሻ አካላትን አድራሻ የያዘ ነው፡፡
በደብሊው ኤ ኤች አሳታሚ የተዘጋጀው የጤና አገልግሎት ማውጫው፤ ተደራሽነቱን ለማስፋት ሲባል በመጽሃፍ መልክ ከመቅረቡ በተጨማሪ በድረ ገጽ እና በሞባይል አፕሊኬሽን አማካይነት ተዘጋጅቶ ለተጠቃሚዎች መቅረቡን አዘጋጁ በተለይ ለአዲስ አድማስ ጠቁሟል፡፡  
ማውጫው በአዲስ አበባ እና በመላ የአገሪቱ ክልሎች ለሚገኙ የጤና ተቋማት በነጻ የሚሰራጭ ሲሆን  ለጤና ተቋማት የመረጃ ምንጭ በመሆን የርስ በርስ ግንኙነትን ከማጎልበት ባለፈ፣ ለጤና አገልግሎት ተጠቃሚዎችም የማንኛውም የጤና ነክ መረጃ ምንጭ በመሆን ያገለግላል፡፡
አዘገጃጀቱ ለተጠቃሚዎች ምቹ በመሆኑና መረጃዎቹ በየጤና ዘርፉ ተከፋፍለው የቀረቡ መሆናቸው፣ የጤና አገልግሎት ተጠቃሚው ህብረተሰብ እንደፍላጎቱና እንደችግሩ የሚበጀውን መረጃ በቀላሉ ለማግኘት እንደሚያስችለው አዘጋጁ ገልጸዋል።
በዝግጅቱ የኢፌዲሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር እና የመድሀኒት የምግብ እና የጤና ክብካቤ ባለስልጣንን ጨምሮ በጤናው ዘርፍ የሚሰሩ መያዶች፣ ሌሎች ባለድርሻ አካላትና በዘርፉ ለአመታት የሰሩ አንጋፋ የህክምናው ዘርፍ ባለሙያዎች፣ ተቋማትና የመንግስት አካላት የተሳተፉ ሲሆን፣ በሚቀጥሉት እትሞችም ተደራሽነቱን በስፋት ለማሳደግ እየተሰራ ነው ተብሏል።
በዘርፉ የሚታየውን የመረጃ ክፍተትን በመሙላት ረገድ ጠቀሜታው የጎላ እንደሆነ የተነገረለት የጤና አገልግሎት ማውጫው፣ የኢፌዲሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስትር ልዩ ጽ/ቤት ሃላፊ ዳይሬክተር ጀነራል፣ የጤናው ዘርፍ ባለድርሻ አካላትና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ባለፈው ሃሙስ በኢትዮጵያ ሆቴል በተዘጋጀ ፕሮግራም ላይ በይፋ ተመርቋል፡፡


Saturday, 16 May 2015 10:53

የሰዓሊያን ጥግ

(ስለ ፎቶግራፍ)

ብርሃን ባለበት ሁሉ ፎቶግራፍ ማንሳት ይቻላል፡፡
አና ጊዴስ
ጥሩ ፎቶግራፍ ማለት የቱ ጋ እንደምትቆም ማወቅ ነው፡፡
አንሴል አዳምስ
ፎቶግራፍ ማንሳት ከህይወት ጋር የሚደረግ የፍቅር ግንኙነት ነው፡፡
ቡርክ ዩዝል
አካባቢውን እስክትለቅ ድረስ ካሜራህን አትሸክፍ፡፡
ጆ ማክናሊ
ፎቶግራፍ ማንሳት አንዴ ደም ስርህ ውስጥ ከገባ እንደ በሽታ ነው፡፡
አኖን
እጄ ላይ ካሜራ ሲኖር ፍርሃት አላውቅም፡፡
አልፍሬድ አይዞንስታዴት
የሰውን ፊት በትክክል የሚያየው ማነው? ፎቶግራፍ አንሺው ነው? መስተዋቱ ነው? ወይስ ሰዓሊው?
ፓብሎ ፒካሶ
በአሜሪካ ፎቶግራፍ አንሺ የተከሰተውን የሚቀርፅ ብቻ አይደለም፤ የሚፈጥርም ጭምር እንጂ፡፡
ሱሳን ሶንታግ
ቃላትን አላምንም፤ የማምነው ምስሎችን ነው፡፡
ጊሌስ ፔሬስ
ትኩረቴን የሚስበው ፎቶግራፍ ራሱ አይደለም፡፡ እኔ የምፈልገው የተጨባጩን ዓለም አንድ ደቂቃ ማስቀረት ብቻ ነው፡፡
ሔነሪ ካርቲየር ብሪሶን
ተመልከቱ! ምሁር አይደለሁም - ምስሎችን ብቻ ነው የማነሳው፡፡
ሔልሙት ኒውተን
ድንቅ ፎቶግራፍ የስሜት ጥልቀት እንጂ የመስክ ጥልቀት አይደለም፡፡
ፒተር አዳምስ
የእኔ ተወዳጅ ፎቶግራፎች የትኞቹ ናቸው? ነገ የማነሳቸው!!
አይሞገን ከኒንግሃም
ጥሩ ፎቶግራፍ አንዲትን ቅፅበት ከማምለጥ ይገታታል፡፡
ኢዩዶራ ዌልቲ

ላለፉት አምስት አመታት በአፍሪካ ህብረት የኤርትራ ልኡክ ሆነው ያገለገሉትና ከአገሪቱ ከፍተኛ ዲፕሎማቶች አንዱ የሆኑት አምባሳደር ሞሃመድ ኢድሪስ ጃዊ፤ የኤርትራ መንግስት በዜጎቹ ላይ የሚፈጽመውን ጭቆናና የመብቶች ጥሰት በመቃወም በኢትዮጵያ ጥገኝነት መጠየቃቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ፍትህና ነጻነትን ለመጎናጸፍ ለዘመናት የታገለው የኤርትራ ህዝብ፤ በኢ-ፍትሃዊ አገዛዝ ስር እየማቀቀ ይገኛል ያሉት አምባሳደሩ፤ ይህም የኤርትራን መንግስት የጭቆና አገዛዝ በመቃወም በኢትዮጵያ ጥገኝነት ለመጠየቅ ውሳኔ ላይ እንዳደረሳቸው ተናግረዋል፡፡
በኤርትራ የነጻነት ትግል ዘመናት በትግል ያሳለፉት አምባሳደር ሞሃመድ፤ኤርትራ ነጻነቷን ከተጎናጸፈች  በኋላም በተለያዩ ከፍተኛ የስልጣን ቦታዎችና በአህጉራዊ የዲፕሎማቲክ ስራዎች ላይ ለአመታት ማገልገላቸው ተነግሯል፡፡
የመብት ተሟጋች ቡድኖችና የተለያዩ ተቋማት፣ የኤርትራ መንግስት በመብቶች ጥሰትና በአስገዳጅ የወታደራዊ አገልግሎት ዜጎቹን እያሰቃየ ነው ሲሉ አገዛዙን ቢተቹም፣ የኤርትራ መንግስት ግን የሚሰነዘሩበትን መሰል የመብቶች ጥሰት ውንጀላዎች በተደጋጋሚ እንደሚያጣጥል አስታውሷል፡፡
የኤርትራ መንግስት ባለስልጣናት በአምባሳደሩ የጥገኝነት ጥያቄ ዙሪያ ያላቸውን አስተያየት እንዲሰጡት ያደረገው ሙከራ እንዳልተሳካለት ሮይተርስ ገልጧል፡፡