Administrator

Administrator

“የተሻለ ኮንስትራክሽን፣ ለተሻለች ኢትዮጵያ”


የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ሥራ ተቋራጮች ማህበር በየዓመቱ የሚያዘጋጀው “ኢትዮ ኮን” ዓለም አቀፍ የኮንስትራክሽን ኤግዚቢሽን ባለፈው ረቡዕ በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል የተከፈተ ሲሆን ነገ አመሻሽ ላይ ይጠናቀቃል ተብሏል። “የተሻለ ኮንስትራክሽን፣ ለተሻለች ኢትዮጵያ” በሚል መሪ ቃል በተከፈተው በዚህ ኤግዚቢሽን ላይ ከ100 በላይ የአገር ውስጥና የውጭ የኮንስትራክሽን ኩባንያዎች የተሳተፉ ሲሆን ከውጭዎቹ ሀገራት፡- ቻይና ቱርክ፣ ህንድ፣ ደቡብ ኮሪያና ሌሎችም ተሳታፊ መሆናቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በኤግዚቢሽኑ ላይ የኮንስትራክሽን እቃ አምራቾች፣ አቅራቢዎች፣ ዲዛይንና ስፔስፊኬሽን አዘጋጆች፣ ስራ ተቋራጮች፣ የሪል እስቴት አልሚዎች፣ ኤጀንቶች፣ የኮንስትራክሽን ማሽነሪ የአገር ውስጥ አምራቾች፣ አስመጭና አከፋፋዮች እንዲሁም ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል፡፡
የኢትዮጵያ የኮንስትራክሽን ሥራ ተቋራጮች ማህበር ፕሬዚዳንት ኢ/ር አበራ በቀለ በመክፈቻው ላይ ባደረጉት ንግግር፤ በኢትዮጵያ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ የመጣው የኮንስትራክሽን ዘርፍ፣ እድገቱ ጤናማና ትክክለኛ እንዲሆን ለማድረግ፣ ሀላፊነቱ የዘርፉ ባለድርሻ አካላት ቢሆንም በዋናነት ከዘርፉ ባለቤት ከኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ብዙ እንደሚጠበቅ ጠቁመው፣ አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ኤግዚቢሽኑ ምርትና አገልግሎትን ለጎብኚ በማቅረብ ብቻ ሳይወሰን የውይይት መድረክም አዘጋጅቷል፡፡ በዛሬው ዕለት ከጠዋቱ 2፡30 ጀምሮ በኢሲኤ አዳራሽ፤ “ወቅታዊ የኢትዮጵያ የኮንስትራክሽን ሥራ ተቋራጮች ተግዳሮቶችና የእድገት ማነቆዎች”፣ “የቴክኖሎጂ ሽግግር በካፒታል ኢንተንሲቭ፣ በኮንስትራክሽን ዘዴ”፣ “የኮንስትራክሽን ግዢና የኮንስትራክሽን አስተዳደር”፣ “ብክነትና ሊን ኮንስትራክሽን” በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ጥናታዊ ፅሁፎች ቀርበው  ውይይት እንደሚካሄድ ለማወቅ ተችሏል፡፡

አዲስ አበባ የጤናና የቢዝነስ ኮሌጅ፣ ለ13ኛ ጊዜ በዲግሪና በደረጃ አራት ያሰለጠናቸውን 429 ተማሪዎች ባለፈው ሳምንት በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ አስመረቀ።ተመራቂዎቹ በነርሲንግ፣ በጤና መኮንን፣ በክሊኒካል ነርሲንግና በላብራቶሪ ቴክኒሺያን የትምህርት ዘርፍ
የሰለጠኑ እንደሆኑ ታውቋል፡፡ኮሌጁ ከተመሰረተበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን ድረስ በሶማሌ ላንድ ሀርጌሳ የሚገኘውን ካምፓስ ጨምሮ
በአዲስ አበባና በተለያዩ ክልሎች ባሉት ካምፓሶቹ፣ከ47ሺህ በላይ የህክምና ባለሙያዎችን አሰልጥኖ በማስመረቅ በጤናው ዘርፍ ያለውን የባለሙያ ክፍተት ሲሞላ መቆየቱን የኮሌጁ ባለቤትና ፕሬዚዳንት ተናግረዋል፡፡ ከተመረቁ 47 ሺህ ባለሙያዎች መካከል
ከ10 ሺህ በላይ የሚሆኑት በኮሌጁ ነፃ የትምህርት እድል ተጠቃሚዎች እንደነበሩ ያስታወሱት ፕሬዚዳንቱ፤
በየካምፓሶቹ በዓመት ለ20 ተማሪዎች ነፃ የትምህርት እድል እንደሚሰጥና በተለይ መክፈል ባለመቻል መማር ላልቻሉ ሴት ልጆች ቅድሚያ በመስጠት ኃላፊነቱን ሲወጣ እንደቆዩ አክለው ገልፀዋል፡፡ተማሪዎች እዚህ ትምህርታቸውን አጠናቅቀው ለከፍተኛ ትምህርት አሜሪካ በሚሄዱበት ወቅት ተቀባይነት የሚያስገኝ፣ በአሜሪካ እውቅና ያለው ብቸኛ ኢትዮጵያዊ ኮሌጅ መሆኑን ፕሬዚዳንቱ በምርቃቱ ዕለት አስታውቀዋል

በብርሀኑ ደጀኔ የተሰናዳውና በእውነተኛ ታሪኮች ላይ ያጠነጥናል የተባለው፣ “በራስ እይታ የእማዬ ውለታ” መፅሀፍ ለንባብ በቃ።መፅሀፉ፤ የልጅነት፣ የስራ፣ የት/ቤትና ተለያዩ የህይወት አጋጣሚዎችን ያስቃኛል፤ ተብሏል። በ74 ገጽ የተመጠነው መፅሀፉ፣ በ70 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

Monday, 25 September 2017 11:56

የዒላማ ግርዶሽ

ርዕስ የለሽ ጽሕፈት
ውል አልባ ምዕራፍ
የምገርፈው በሬ
የሚጮኸው ጅራፍ
ያገር ደጅ ስጠና
ተከፈተ በራፍ፡፡
ክፋት ላይ ስተኩስ
ቅንነት ተመታች
ለተኩላ ባለምኩት
እርግብ በ’ራ ገባች
እርኩስ መቺ ቀስቴ
ደግ ላይ ተሰካች፡፡
ባላሚ ታላሚ
መሀል ስቶ ገብቶ
የዒላማ ግርዶሽ
ባገር ተንሰራፍቶ
አልሞ ለመምታት
አልተቻለም ከቶ፡፡
ከምሥጋና ጋር
ሳምሶን ጌታቸው ተ/ሥላሴ

* የቅዱስ ላሊበላ ደብርንና የደብረ ሊባኖስ ገዳምን ይጐበኛሉ
* ከፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ ጋር እንደሚነጋገሩ ይጠበቃል

     የሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ቅዱስ ባስልዮስ ማር ቶማ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ የፊታችን ማክሰኞ በሚከበረው የመስቀል ደመራ በዓል ላይ ለመገኘት ከነገ በስቲያ ቀትር ላይ አዲስ አበባ የሚገቡ ሲሆን ከርእሰ ብሔሩ ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ ጋራ ተገናኝተው እንደሚነጋገሩ ተጠቁሟል፡፡
ቅዱስ ፓትርያርኩ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን አምስት ልኡካን በመምራትም፣ በኢትዮጵያ የአራት ቀናት ጉብኝት እንደሚያደርጉ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡
ለጉብኝቱ በወጣው መርሐ ግብር መሠረት፥ ሰኞ፣ ከቀትር በኋላ፣ የህንዱ ፓትርያርክ፣ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ኦፌሴላዊ አቀባበል ይደረግላቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱና የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ሊቃውንት፣ የሰንበት ት/ቤት አባላትና ምእመናን በተገኙበት በሚደረገው አቀባበል፣ ፓትርያርኩ፣ ትምህርተ ወንጌል ይሰጣሉ፤ ተብሏል፡፡
በማግሥቱ ማክሰኞ፣ ከርእሰ ብሔሩ ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ ጋራ ተገናኝተው እንደሚነጋገሩ የተጠቀሰ ሲሆን፤ ከቀትር በኋላም፣ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ጋራ ወደ መስቀል ዐደባባይ በማምራት፣ የደመራን በዓል ያከብራሉ፡፡ ብዙ ሺሕ የሰንበት ት/ቤቶች ወጣቶች የሚያቀርቡትንና የሥነ በዓሉ ድምቀት የሆነውን ዐውደ ትርኢት የሚመለከቱት የህንዱ ፓትርያርክ፤ የሁለቱን አገሮችና አብያተ ክርስቲያናት ጥንታዊ ወዳጅነትና ቀጣይ ግንኙነት የተመለከተ ንግግር የሚያደርጉ ሲሆን ደመራውን፣ ከፓትርያርክ አቡነ ማትያስና ከአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ድሪባ ኩማ ጋራ በአንድነት እንደሚለኩሱ ተጠቁሟል፡፡
በዕለተ ረቡዕ የመስቀል በዓልን፣ በላሊበላ ደብር ውቅር አብያተ ክርስቲያናት በመገኘት እንደሚያከብሩም የተገለጸ ሲሆን ከዚያም መልስ፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ቤተ መጻሕፍት ወመዘክርን፣ የሰበታ ጌቴሰማኔ ቤተ ደናግል ሴቶች ገዳምንና የደብረ ሊባኖስ ገዳምን እንደሚጎበኙ መርሐ ግብሩ ያስረዳል። ከጉብኝታቸው ፍጻሜ በኋላ፣ በሁለቱ እኅትማማች አብያተ ክርስቲያናት አንድነትና ዓለም አቀፍ አገልግሎት ዙሪያ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ ደረጃ የጋራ ምክክር እንደሚያካሒዱና መግለጫም እንደሚሰጡ ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ ባለፈው ዓመት ኅዳር ሕንድን በጎበኙበት ወቅት ባቀረቡላቸው ግብዣ መሠረት፣ መስቀል ደመራን በኢትዮጵያ የሚያከብሩት ቅዱስ ባስልዮስ ማር ቶማ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ ለመጀመሪያ ጊዜ ከተገኙበት የካቲት ወር 2005 ዓ.ም. በዓለ ሢመት ወዲህ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ የሚያደርጉት ጉብኝት እንደሆነና የሁለቱን አብያተ ክርስቲያናት የተጠናከረ ግንኙነት እንደሚያሳይ ተጠቅሷል፡፡
ከቀድሞም ጀምሮ በአገራችን ዘመናዊ ትምህርት ቤቶች ጎልቶ የሚታየው የሕንዳውያን መምህራን አገልግሎት፣ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሥነ መለኰት ኮሌጆችም መኖሩን ምንጮቹ አስገንዝበዋል፡፡ በአንጋፋው የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በማስተማር የሚታወቁ ዕውቅ የሥነ መለኰት ሊቃውንትን ያወሱት ምንጮቹ፤ ኮሌጁ በቀድሞው መንግሥት ተዘግቶ ዳግም ከተከፈተበት ከ1987 ዓ.ም. ወዲህም አገልግሎታቸው መቀጠሉንና ከመምህራኑም  መካከል ለማዕርገ ጵጵስና የበቁ እንዳሉ ጠቅሰዋል። ይህም፣ የቆየውን ግንኙነትና ትብብር ለማጠናከር ከፍተኛ ሚና መጫወቱን አስረድተዋል፡፡
ቅዱስ ባስልዮስ ማር ቶማ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ እ.ኤ.አ ከኖቨምበር 2010 ጀምሮ፣ በሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ቶማስ የተሠየሙ 91ኛው የምሥራቅ ካቶሊኮስና የማላንካራ መጥሮጶሊጣን ናቸው፡፡ በኦፊሴላዊ ስያሜዋ፣ የማላንካራ ኦርቶዶክስ ሶርያ ቤተ ክርስቲያን ወይም የኦርቶዶክስ ሶርያዊ ምሥራቅ ቤተ ክርስቲያን ተብላ የምትጠራው የሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን፣ በሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ በ52 ዓ.ም. የተመሠረተች ጥንታዊት ናት፡፡ በደቡብ ሕንድ የምትገኘው ኬሬላ ወይም ማላንካራ፣ የክርስትናው መሠረት የተጣለባት የመንበሩ መቀመጫ ስትሆን፤ ካቶሊኮስ የሚለው የርእሰ መንበሩ ሥያሜም የፓትርያርክ አቻ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ በአሁኑ ወቅት ቤተ ክርስቲያኒቱ፣ በሊቃነ ጳጳሳት የሚመሩ 25 የሀገር ውስጥና የውጭ አህጉረ ስብከትን እንዳቋቋመችና ከ2.5 ሚሊዮን በላይ ተከታዮች እንዳሏት መረጃዎች ያሳያሉ፡፡
በሌላ በኩል፣ ትውልደ ሕንዳውያንና የኦርቶዶክስ ክርስትና ተከታይ የሆኑ በርካታ ተሳላሚዎች፣ የሕንዱን ፓትርያርክ በመከተል በአዲስ አበባ የመስቀል ዐደባባይ ተገኝተው የደመራን በዓል እንደሚያከብሩ ታውቋል። ነዋሪነታቸውን በሕንድ፣ በአሜሪካና በእስራኤል ያደረጉ መነኰሳትን፣ ካህናትንና ምእመናንን ያካተተውና በአርባ አምስት ቡድን የተደራጀው ይኸው የተሳላሚዎቹ መንፈሳዊ ጉዞ፣ በአንጋፋው የሙምባዩ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ የሚመራ እንደሆነ ተነግሯል፡፡ የጠቅላይ ጽ/ቤቱ ምንጮች እንደገለጹት፣ ተሳላሚዎቹ፣ “በኢትዮጵያ ገዳማት ሥርዓትና አኗኗር ዝና ተስበው የመጡ መንፈሳውያን ተጓዦች ናቸው፡፡” በኒውዴልሂ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቢሮ አስተባባሪነት በተዘጋጀው ጉብኝት ፓኬጅ መሠረትም፣ የደመራን በዓል በመስቀል ዐደባባይ ተገኝተው ያከብራሉ፤ የላሊበላ ደብር ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን፣ የጣና ገዳማትንና የጠቅላይ ጽ/ቤቱን ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር ይጎበኛሉ፤ ብለዋል - ምንጮቹ፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንድ እናት ቢምቢ ትንኝና ልጅ ቢንቢ ትንኝ ነበሩ፡፡ ልጅዬዋ ቢምቢ፤ በአገሩ እየተዘዋወረች ዙሪያ ገባው ውስጥ ነዋሪ - የሆኑትን እንስሳት፣ አዕዋፍና ነብሳት ልትጠይቃቸው ጎራ ልትል አሰበች፡፡ ይህንን ያወቀችው እናት፤
“መሄዱንስ ሂጂ፡፡ ዘመድ ማግኘትና መጠየቅ በጣም ጥሩ ነው፡፡ ነገር ግን ወዳጅና ጠላትሽን መለየት ይኖርብሻል፡፡ ጠላት የመሰለሽ ወዳጅ ሆኖ ይገኛል፡፡ ወዳጅ ያልሺው ደግሞ፣ ጠላት ሆኖ ተለውጦ ታገኚዋለሽ። ለማንኛውም ማጣራትን የመሰለ ነገር የለም፡፡”
ልጅዬዋ ቢምቢም፤
“እሺ እማማ፣ ቀስ ብዬ እያጣራሁ ለማየት እሞክራለሁ” ብላ አካባቢዋን ልታጠና መንገድ ቀጠለች፡፡
መጀመሪያ ቢራቢሮን አገኘች፡፡ “ቢራቢሮ እንደምነሽ?”
ቢራቢሮ፤
“ደህና ነኝ” አለች፡፡
“በአካባቢው ያሉ ነብሳት ተስማምተውሽ ይኖራሉ?”
“አዎን፡፡ ግን ክረምትም በጋም ሳልቸገር ለመኖር በመቻሌ፣ ወረተኛ ነሽ እያሉ ይወቅሱኛል”
“እነሱ ምን ፈልገው ነው?”
“ወይ የበጋ ሁኚ ወይ የክረምት ሁኚ ነው የሚሉኝ”
“ቆይ፤ ስለዚህ ጉዳይ እናቴን ጠይቄ ምን እንደምትል እነግርሻለሁ” ብላት ቢምቢ ሄደች፡፡
ቀጥላ ጦጣን አገኘቻት፡፡
“ጦጢት እንደምንድነሽ?”
“ደህና ነኝ”
“ከእንስሳቱ ጋር ስትኖሪ ምን ችግር ገጥሞሽ ያውቃል?”
“ምንም ችግር አልገጠመኝም፡፡ ግን ሁሉም በአንድነት በእኔ ላይ ፈርደው ብልጣ - ብልጥ ብትሆኚ ምን አለበት ታዲያ?”
“ታታልይኛለሽ፡፡ ታሞኚኛለሽ እያሉ ነው፡፡”
“የራሳቸው ጅልነት ነው ተያቸው” ብላ ቢምቢ መንገድ ትቀጥላለች፡፡
ብዙም ሳትሄድ አንበሳን አገኘችው፡፡
ቢምቢ፤
“ደህና ዋልክ አያ አንበሶ?”
“ደህና ነኝ፤ ቢምቢ”
“እንስሳት አብረውህ ሲኖሩ ምን ይሉሃል?”
“ጉልበተኛ ነህ፡፡ አምባገነን ነህ፤ ነው የሚሉኝ” አለ እየተጎማለለ፡፡
“አቅም ስላነሳቸው ነው እነሱ፡፡ ተዋቸው፡፡” ብላው መንገዷን ቀጠለች፡፡
በመጨረሻ የተሰበሰቡ ሰዎች አግኝታ፣ እነሱን አዳመጠችና፣ እየመሸ ስለመጣ ወደ እናቷ ተመለሰች፡፡
የሆነችውን ሁሉ ነገረቻት፡፡
“ሰዎችስ ምን አሉሽ?” አለቻት እናት ቢምቢ፡፡
ልጅየዋ ቢምቢም፤
“ይገርምሻል፤ ሰዎችማ ሲያጨበጭቡልኝ ዋሉ” አለቻት፡፡
እናት ቢምቢም፤
“ልጄ ሁለተኛ እንዳትሳሳቺ! እንደ፣ሰዎች ክፉ የለም፡፡ ያጨበጨቡልሽ የመሰለሽም በመዳፍና መዳፋቸው ጨፍልቀው ሊገድሉሽ ሲሞክሩ ነው፡፡ ስለዚህ ዳግመኛ እንዳትታለይላቸው!” አለችና መከረቻት፡- “ማጨብጨብ የሰው ልጆች ኃይለኛ መሳሪያ ነው፤ ተጠንቀቂ!”
*           *           *
አክራሪ መሆን መጥፎ የመሆኑን ያህል አድር - ባይና ወላዋይ መሆንም ያንኑ ያህል አስቸጋሪ ጠባይ ነው! ብልጣ ብልጥ መሆን የራሱ ችግር እንዳለው ሁሉ፣ ሞኛ - ሞኝ መሆንም ለማንም ብልጥ - ነኝ - ባይ የማታለል ተግባር ሰለባ ስለሚያደርግ፤ መጠንቀቅ ተገቢ ነው! አምባገነንነት ሁልጊዜ አያበላም፡፡ በእርግጥም የተገፉ፣ የተበደሉ፣ ፍትሕ - ያጡ፣ የተመረሩ ህዝቦች በተነሱ ጊዜ ማናቸውም ፈላጭ - ቆራጭ አገዛዝ አሳሩን ያያል፡፡ በዓለም ላይ ስንት አምባገነኖች ተሰባብረው እንደወደቁ ማሰላሰል ነው! የደገፉ መስለው ጧት ማታ ሲያጨበጭቡልን ጤነኛ መስለውን፤ “አሁን ነው ራስን ማሳየት” ብሎ ብቅ ማለት አደጋ አለው! ለመውረድ ብዙ ሽቅብ መውጣትም ክፉ ባህሪ ነው፡፡ ሁሉን፣ ሁልጊዜ አገኛለሁ ማለትም ግብዝነት ነው፡፡ እያጨበጨቡ ጎል ከሚከቱን ይሰውረን!
ዛሬ የትምህርት ጊዜ ነውና ትምህርታችንን ይግለጥልን፡፡ እንደ እስያ፤ “ዕውቀት እያለ የሚማር ጠፋብን” የሚል ትራጀዲ ውስጥ እንዳንገባ አምላክ ይጠብቀን!
“ምዕራቡ ዓለም ሲያስነጥስ ሌላው ክፍለ ዓለም ኒሞኒያ ይይዘዋል” የሚለውን በማሰብ፤ እንዳይምታታብን ራሳችንን እንቻል! የራስን የመሰለ ምንም ነገር የለም፡፡
የመጨረሻው እንግሊዛዊ የህንድ ገዢ ሎርድ ሉዊ፣ ለማህታማ ጋንዲ እንዲህ አለው “እኛ ከወጣን በህንድ አገር ቀውስ ይፈጠራል!”
ይሄኔ ማህታማ ጋንዲ፤
“አዎን ቀውስ ይፈጠራል - ቀውሱ ግን የራሳችን ነው!” አለና፤ ኩም አደረገው፡፡
“የራሳችንን ቀውስ ‘ራሳችን እንፈታዋለን!”
አንድ ፀሐፊ ካነበብናቸው በርካታ መጣጥፎች አንዱ ላይ፤ “የአዕምሯችን ማዕከል፣ እና ደጃፉም ሆነ ግንባሩ በጣም ሩቅ ለሩቅ ናቸው! ግን ተቀናጅተው ሥራ ይሰራሉ” ይላል፡፡ የእኛም ተግባር እንደዚሁ የተቀናጀ መሆን ይኖርበታል! ከተሳሰብንና ከተናበብን የስሌት ስህተት አንሰራም፡፡ የፍርድ ማዛባት ስህተት አንሰራም፡፡ የመረዳዳት ማቃት ስህተት አንሰራም፡፡
ዛሬ “ነፃ ኢኮኖሚ”፣ “ዲሞክራሲ”፣ “መልካም አስተዳደር” አስፈላጊ ነው ብለን ተፈጥመናል፡፡ ያም ሆኖ የፌደራሊዝምን ስርዓት፣ በተለይ የብሔር ብሔረሰብን ፌደራሊዝም ጨርሶ ካላደገው ካፒታሊዝማችን ጋር አብረን ለማስኬድ ብዙ እንቅፋት ሲፈጠርብን ይታያል፡፡ ኦሊቨር ጎልድስሚዝ የተባለው ገጣሚ፤ “ሀብት ይከማቻል ሰው ይበሰብሳል” ወደ ውስጥ እያየን፣ ራሳችንን እንፈትሽ፡፡ ነፃ ኢኮኖሚ ስንል በምን የዕድገት ደረጃ ላይ ላለ ኢኮኖሚ ነው ያጨነው? ብለን እንጠይቅ፡፡ ዲሞክራሲ ስንል በምን ደረጃ ላለ አገር ነው ያስቀደድነውና ስፌቱን የምንመርጠው? እንበል፡፡ ከፊውዶ ቡርዥዋ ሥርዓት ገና ሙሉ ለሙሉ ባልተላቀቀ ፖለቲካል-ኢኮኖሚ ላይ መልካም አስተዳደርን መጋለብ ቀርቶ መፈናጠጥስ ይቻላል ወይ? ብለን እንጠይቅ! ታላቅ ኃይል ያዘለውን ካፒታሊዝም፤ ከማህበረሰባዊ ኮንሰርቫቲዝም ጋር ማጋባትስ አማራጭ ይሆናል ወይ? (ምናልባት የቻይናን፣ የህንድን ስነልቦና ቢሰጠን) ብለን እንመርምር፡፡
የንድፈ-ሀሳብ መንገዳችን ከረኮንች ነው፡፡ እንኳንስ አስፋልት ኮብል-ስቶኑም ገና እያንገዳገደን ነው፡፡ ቆም ብሎ የሚያስብ አስተዋይ አዕምሮ አሁንም ያስፈልገናል! ከዕለታት አንድ ቀን የያዝነው ቲዎሪ ስህተት ሆኖ ቢሆንስ? ብለን መጠያየቅ አይከፋም፡፡ ለሁሉም ህመም አንድ መድኃኒት በመስጠት (ፓናሲያ እንዲሉ) ፈውስ እናገኛለን ብሎ ማሰብ ቀቢፀ- ተስፋ ነው፡፡ ማርክ ትዌይን፤ “መዶሻ ያለው ሰው፣ እያንዳንዱ ችግር ሚሥማር ይመስለዋል!” የሚለው በእኛ ዓይነቱ ላይ ሲሳለቅ ነው፡፡ ከዚህም ይሰውረን፡፡
ለክርስትና ዕምነት ተከታዮች መልካም የመስቀል በዓል!  

      ሚዩዚክ ሜይዴይ ከኢትዮጵስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር፣ ነገ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ በብሄራዊ ቤተ መፃህፍትና ቤተመዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ፣ በአለቃ ዘነበ እና በአለቃ ወልደማሪያም በተፃፉ የአፄ ቴዎድሮስ ዜና መዋዕሎች ላይ ውይይት ያካሂዳል፡፡ ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት ገጣሚና ደራሲ ይታገሱ ጌትነት ሲሆን በዝግጅቱ ላይ ለመሳተፍ ፍላጎት ያለው ሁሉ እንዲሳተፍ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ጋብዟል፡፡

ባለፈው ሰኞ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት አዲስ ማዕቀብ የተጣለባት ሰሜን ኮርያ፣ ይህ ማዕቀብ እንዲጣልብኝ ቁልፍ ሚና ተጫውተዋልና እቀጣቸዋለሁ በሚል፣ “ጃፓንን በውሃ ማዕበል አሰምጣለሁ፣ አሜሪካን ደግሞ ዶግ አመድ አደርጋለሁ” ስትል መዛቷን ዘ ጋርዲያን ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት፣ በቅርቡ ካደረገቺው የኒውክሌር ሙከራ ጋር በተያያዘ በሰሜን ኮርያ ላይ ባለፈው ሰኞ አዲስ ማዕቀብ መጣሉን ያስታወሰው ዘገባው፤ የአገሪቱ መንግስት የውጭ ግንኙነት ኮሚሽንም ይህን አድርጋለች በሚል በአሜሪካ ላይ ከተለመደው በተለየ መልኩ ጠንከር ያለና ብዙዎችን ያነጋገረ ዛቻ መሰንዘሩን ገልጧል፡፡
የሰሜን ኮርያ መንግስት የዜና ወኪል ሃሙስ ዕለት ባሰራጨው ዘገባ፤ የሰሜን ኮርያ መንግስት አራት የጃፓን ደሴቶችን በኒውክሌር ቦንብ ጥቃት ውሃ ውስጥ እንደሚያሰምጥና አሜሪካንም በከፍተኛ ጥቃት ዶግ አመድ እንደሚያደርግ አስታውቋል፡፡
ይህን ተከትሎ የጃፓን መንግስት ቃል አቀባይ፣ የሰሜን ኮርያን ዛቻ “ጸብ አጫሪና እጅግ አደገኛ” በሚል ማውገዛቸውንና ዛቻው በአካባቢው ያለውን ውጥረት የሚያባብስና ተቀባይነት የሌለው ነው በሚል ማጣጣላቸውንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡
ዘ ኢንዲፔንደንት በበኩሉ፣ 15 አባላት ያሉት የተመድ የጸጥታው ምክር ቤት፣ ሰሜን ኮርያ የጨርቃ ጨርቅ ምርቶችን ወደ ውጭ አገራት እንዳትልክ የሚከለክለውንና በአሜሪካ የረቀቀውን የማዕቀብ ሃሳብ ባለፈው ሰኞ ማጽደቁ በአካባቢው ያለውን ውጥረት የበለጠ እንዳባባሰው ዘግቧል፡

 ሳምሰንግ በመሪነቱ ሲቀጥል፣ አፕል ወደ 3ኛ ደረጃ ዝቅ ብሏል

     የቻይናው የቴሌኮም ኩባንያ ሁዋዌ፣ አይፎንን በሚያመርተው የአሜሪካው አፕል ለዓመታት ተይዞ የነበረውን የአለማችን የስማርት ፎን ሽያጭ የሁለተኛነት ደረጃ መረከቡን የእንግሊዙ ቴሌግራፍ ዘግቧል፡፡
ሁዋዌ ባለፉት ሰኔ እና ሐምሌ ወራት ያስመዘገበው የስማርት ፎን ሽያጭ ከአፕል ብልጫ በማሳየት ወደ ሁለተኛነት ደረጃ ከፍ ማለቱን ከሰሞኑ ይፋ የተደረገን የገበያ ጥናት ጠቅሶ ያመለከተው ዘገባው፤ ይህም ሆኖ ግን አፕል በጉጉት ሲጠበቁ የነበሩ አዳዲስ የአይፎን ሞዴሎችን በዚህ ሳምንት ለገበያ ከማቅረቡ ጋር በተያያዘ፣ ሽያጩን ከፍ አድርጎ ወደ ቀድሞ ደረጃው ሊመለስ እንደሚችል ይጠበቃል ብሏል፡፡
ሁዋዌ ለዚህ ስኬት የበቃው በስማርት ፎን ምርት ኢንዱስትሪው፣ በሰፋፊ የገበያና የማስታወቂያ ስራዎችና በሽያጭ መስመሮች ማስፋፊያ ዘርፎች ላይ በቋሚነት ትልቅ ኢንቨስትመንት በማድረጉ ነው መባሉንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
ኩባንያው ከቅርብ አመታት ወዲህ በአለማችን የስማርት ፎን ገበያ ሽያጭ መሪነቱን ከያዘው የደቡብ ኮርያው ሳምሰንግ ጋር ለመፎካከር ብርቱ ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ ያስታወሰው ዘገባው፤ በኔትወርክ ዝርጋታና በሌሎች ተያያዥ መስኮች ላይ ከነበረው እንቅስቃሴ ወደ ስማርት ፎን ምርት በመዞር ወደ ገበያው ከገባ አጭር ጊዜው ቢሆንም፣ በፍጥነት በማደግ ከታላላቆቹ ሳምሰንግ እና አፕል ጋር ለመፎካከር መብቃቱን ገልጧል፡፡
አፕል ኩባንያ እ.ኤ.አ ከ2010 አንስቶ በአለማችን የስማርት ፎን ሽያጭ ገበያ፣ ከአንደኛ ወይም ከሁለተኛ ደረጃ ዝቅ ብሎ እንደማያውቅም ዘገባው አክሎ አስታውሷል፡፡

  ከዚህ በፊትም ፕሬዚዳንቱን በስልጣን ለማቆየት ህገ መንግስቱ ተሻሽሏል

        በኡጋንዳ የገዢው ፓርቲን የሚወክሉ የፓርላማ አባላት፣ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት የዕድሜ ጣራ 75 አመት እንዲሆን የሚገድበውን የህገ መንግስት አንቀጽ እንዲሰረዝ የሚጠይቀውን የውሳኔ ሃሳብ ባለፈው ማክሰኞ በሙሉ ድምጽ መደገፋቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
የፕሬዚዳንቱን የእድሜ ገደብ ለማስቀረት ያለመው የውሳኔ ሃሳቡ፣ የአገሪቱን ህገ መንግስት በማሻሻል፣ የ72 አመቱን ፕሬዚዳንት ዮሪ ሙሴቬኒ፣ በ2021 በሚካሄደው ቀጣዩ የአገሪቱ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንዲወዳደሩ ለማስቻል የተደረገ ሙከራ ነው ሲሉ ተቃዋሚዎች ትችት መሰንዘራቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡
ፕሬዚዳንት ሙሴቬኒ በቀጣዩ ምርጫ ዕድሜያቸው ከ75 አመት በላይ ስለሚሆን፣ በህገ መንግስቱ መሰረት፣ ለፕሬዚዳንትነት መወዳደር እንደማይችሉ የጠቆመው ዘገባው፤ ፓርቲያቸው ናሽናል ሬዚዝታንስ ሙቭመንት ግን፣ ያለ አግባብ ህግ በማሻሻል በስልጣን እንዲቆዩ ለማድረግ ዘመቻ መጀመሩን አመልክቷል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ከሁለት ወራት በፊት በጉዳዩ ላይ በሰጡት አስተያየት፣ አሁን የዕድሜ ገደብን በተመለከተ የምንወያይበት ጊዜ ላይ አይደለሁም፣ አገር በመምራቱ ላይ ነው ትኩረት የማደርገው ሲሉ መናገራቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡
የዕድሜ ገደቡን የሚያነሳው የውሳኔ ሃሳብ በፓርላማው የሚጸድቅ ከሆነ፣ የፕሬዚዳንት ሙሴቬኒን ስልጣን ለማራዘም ሲባል 20 አመታትን ባስቆጠረው የአገሪቱ ህገ መንግስት ላይ የተደረገ ሁለተኛው ማሻሻያ እንደሚሆን የጠቆመው ዘገባው፤ በ2005 ላይም ሙሴቬኒን በስልጣን ላይ ለማቆየት ሲባል ከሁለት የስልጣን ዘመን በላይ መግዛትን የሚከለክለው የህገ መንግስቱ አንቀጽ መሻሻሉን አስታውሷል፡፡