Administrator

Administrator

Saturday, 23 December 2017 09:00

ርዕዩን ነጠቋት …!

ርዕዩን ነጠቋት …!

ኢትዮጵያን ሲያስባት፣ ከዘመናቷ ጠልቆ፣
ጭፍን ሐሳቧ ውስጥ፣ እንዳሸመቀች አውቆ፣
ነጯን ከጥቁር ተማጥቆ፣
ግራጫ ዶሴዋን ጠብቆ፣
የ’ኛን ዐስርት ዓመታት፣ በደቂቃ እድሜው
እየኖረው፣
ዓለም አቀፉን ዕውነታ፣ ሀገሩ በልማድ
ስትወቅረው …
ዘመኗን በ’ውቀት አሰፋ፡፡ የነቢይን
ገቢር ወርሶ፣
የኢዮብን ትዕግስት ጽናት፣ ከሰለሞን
ጥበብ ተውሶ፡፡
ርዕዩን ከአድማስ አሻግሮ፣ አምዶቿን
አለት ላይ ተክሎ፣
የልቡን ትጋት አክሎ፣
ሐሳቡን በጥበብ ሸጠ፤ ዕውቀትን
በአዲስ አብቅሎ፡፡
ዛሬ …
ርዕዩን ማነገት ታክቷት፣ እንደ ሰካራም ባልቴት
ሀገሩ ስትንገዳገድ፣
ነጻ ፈቃዷን ሳትኖረው፣ ድንቁርና ሠልጥኖባት
ስትዋጅ መጥፊያዋን መንገድ፣
ልዕልናዋም ረክሶ፣ እርቀ ሰላሙ ተሰውሮባት
ዘረ ሰቧም ተኳረፈ፤
ደም ፍላቷ ተንተክትኮ፣ አኬልዳማዋ ከሚታየው
እንኳንም እሱ ቀድሞ አረፈ፡፡

                                                                          ገዛኸኝ ፀ. ጸጋው

 በሙስሊም አገራት መካከል ትብብርን የመፍጠር ዓላማ ይዞ የተቋቋመው ኦርጋናይዜሽን ኦፍ ኢስላሚክ ኮፕሬሽን ባለፈው ረቡዕ በቱርክ መዲና ኢስታንቡል ባካሄደው አስቸኳይ ጉባኤ ላይ የተሳተፉ 57 የሙስሊም አገራት መንግስታት፣ ዓለማቀፉ ማህበረሰብ ለምስራቃዊ እየሩሳሌም፣ የፍልስጤም መዲናነት እውቅና እንዲሰጥ ጠይቀዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ትራምፕ፣ እየሩሳሌም የእስራኤል መዲና መሆኗን በተመለከተ ላስተላለፉት ውሳኔ የጋራ ምላሽ ለመስጠት ታስቦ በቱርኩ ፕሬዚዳንት ጣይብ ኤርዶጋን በተጠራው አስቸኳይ ጉባኤ ላይ የተሳተፉት የአገራቱ መሪዎች ባወጡት የጋራ መግለጫ፤ ፕሬዚዳንት ትራምፕ ባለፈው ሳምንት ለእየሩሳሌም የእስራኤል መዲናነት የሰጡትን እውቅናም ውድቅ ማድረጋቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
“የትራምፕ ውሳኔ ህጋዊነት የጎደለውና ፍጹም ተቀባይነት የሌለው ነው” በሚል በጋራ ያወገዙት መንግስታቱ፤ አሜሪካ ይህንን ውሳኔዋን እንድትሽር የጠየቁ ሲሆን ይህንን ባለማድረጓ ለሚከተሉት ጥፋቶችና ቀውሶች ሁሉ ሃላፊነቱን ለመውሰድ እንድትዘጋጅም ማስጠንቀቃቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡
የአገራቱ መሪዎች በጉባኤው ማብቂያ ላይ ባወጡት የጋራ መግለጫ፣ አንዳንዶች እንደገመቱት በእስራኤልም ሆነ በአሜሪካ ላይ ምንም አይነት ማዕቀብ አለመጣላቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ይህም ሆኖ ግን የአገራቱ የጋራ አቋም የአሜሪካን ውሳኔና አቋም ያስቀይራል ተብሎ እንደማይጠበቅ ጠቁሟል፡፡
“የትራምፕ ውሳኔ ዓለማቀፍ ህጎችን የሚጥስ ትልቅ ወንጀል ነው፤ እየሩሳሌም የፍልስጤም መዲና ነበረች፤ አሁንም ናት፤ ወደፊትም ሆና ትቀጥላለች” ሲሉ በጉዳዩ ላይ ያላቸውን ጠንካራ አቋም የገለጹት የፍልስጤሙ ፕሬዚዳንት ማህሙድ አባስ፤ “ለእየሩሳሌም የፍልስጤም መዲናነት እውቅና እስካልተሰጠ ድረስ በመካከለኛው ምስራቅ አካባቢ ሰላምና መረጋጋት የሚባል ነገር አይታሰብም” ሲሉም አስጠንቅቀዋል፡፡
የቱርኩ ፕሬዚዳንት ጣይብ ኤርዶጋን በበኩላቸው፤ ሃያላን አገራት እየሩሳሌም የፍልስጤም ዋና ከተማ ለመሆኗ እውቅና እንዲሰጡ ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን “አሜሪካ ይህንን ተገቢነት የሌለው ውሳኔ መሻር ይገባታል” ማለታቸውንም ዘገባው አመልክቷል፡፡

- የብሩንዲው መሪ ስልጣናቸውን ለማራዘም ዘመቻ ጀምረዋል
             - የኡጋንዳው አቻቸውም ስልጣን ላለመልቀቅ ህግ ሊያሻሽሉ ደፋ ቀና እያሉ ነው

    የስልጣን ዘመናቸውን ሊያጠናቅቁ 2 አመታት ብቻ የቀራቸው የብሩንዲው ፕሬዚደንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ ስልጣናቸውን ለማራዘም የሚያስችሏቸውን የህገ መንግስት ማሻሻያዎች በመደገፍ ድምጻቸውን እንዲሰጡ ደጋፊዎቻቸውን የማግባባት ዘመቻ ባለፈው ማክሰኞ መጀመራቸውንና ይህም አገሪቱን ወደ ከፋ ብጥብጥና ቀውስ ሊያስገባት ይችላል የሚል ስጋት መፍጠሩን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱን መሪ የስልጣን ዘመን ገደብ የሚወስነውን የህገ- መንግስት አንቀጽ ለማሻሻል በቅርቡ ህዝበ ውሳኔ እንደሚካሄድ የጠቆመው ዘገባው፤ስልጣናቸውን በወቅቱ ካልለቀቁ በአገሪቱ የባሰ ግጭትና ብጥብጥ እንደሚከሰት ከተቀናቃኞቻቸው ማስጠንቀቂያ ቢደርሳቸውም፣ ንኩሩንዚዛ ግን ጊቴጋ በተባለው የአገሪቱ ግዛት የቅስቀሳ ዘመቻ መጀመራቸውን አመልክቷል፡፡
ህጉ በሚፈቅደው መሰረት ለሁለት የስልጣን ዘመናት አገሪቱን የመሩት ፕሬዚዳንቱ፤ በ2015 ላይ ህገ መንግስቱን በማሻሻል ለሶስተኛ የስልጣን ዘመን በምርጫ ለመወዳደር መወሰናቸውን በይፋ ማስታወቃቸውን ተከትሎ፣ በአገሪቱ በተቀሰቀሰው የከፋ ግጭትና ብጥብጥ በመቶዎች የሚቆጠሩ የአገሪቱ ዜጎች ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡
ንኩሩንዚዛን ለሁለት የስልጣን ዘመናት በመንበራቸው ላይ የሚያቆየውን የህገ መንግስት ማሻሻያ የማድረግ ሃሳቡን ያፈለቀው ፕሬዚዳንቱ መርጦ የሾመው የአገሪቱ ኮሚሽን እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ ራሳቸው የሚመሩት ካቢኔም ሃሳቡን እንዳጸደቀውና ህዝበ ውሳኔው እንዲካሄድ መፍቀዱን አመልክቷል፡፡ የአገሪቱ ዋነኛ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ፕሬዚዳንቱ የጀመሩትን የቅስቀሳ ዘመቻ ያወገዙ ሲሆን ፕሬዚዳንቱ እድሜ ልካቸውን በስልጣን ላይ የመቆየት ጽኑ ፍላጎታቸውን ለማሳካት እስከቻሉ ድረስ አገሪቱ ወደ እልቂትና የእርስ በእርስ ግጭት ብትገባ ግድ እንደሌላቸው ጠቁመዋል፡፡
ለ13 አመታት የዘለቀውን የብሩንዲ ደም አፋሳሽ የእርስ በእርስ ግጭት ለማቆም በሚል እ.ኤ.አ በ2005 የአሩሻው ስምምነት መደረጉን ተከትሎ ስልጣን የያዙት ፕሬዚዳንት ንኩሩንዚዛ፣ በ2010 በተካሄደውና ተቃዋሚዎች ባልተሳተፉበት ምርጫ  አሸንፈው በገዢነት መቀጠላቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ በ2015 ላይም ለሶስተኛ የስልጣን ዘመን እወዳደራለሁ ማለታቸውን ተከትሎ እንዲካሄድ የተወሰነው ህዝበ ውሳኔ  ማሻሻያውን የሚደግፍ ከሆነ፣ ሰውዬው በስልጣን ላይ የቆዩበት ጊዜ በድምሩ 14 አመታት እንደሚደርስ አመልክቷል፡፡
በተያያዘ ዜና፣ የኡጋንዳው ፕሬዚዳንት ዮሪ ሙሴቬኒ፣ የአገሪቱን መሪ የዕድሜ ገደብ በማራዘምና አምስት አመት የነበረውን የፕሬዚዳንቱ አንድ የስልጣን ዘመን ወደ ሰባት አመት ከፍ በማድረግ ስልጣናቸውን ለማስቀጠል ባቀረቡት ረቂቅ ሃሳብ ላይ የአገሪቱ ፓርላማ በቅርቡ ውሳኔ ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ላለፉት ከ30 በላይ አመታት አገሪቱን የገዙት ሙሴቬኒ፤ በቀጣዩ ምርጫ 77 አመት እንደሚሆናቸውና ህጉ ግን ለመሪነት መወዳደር የሚችለው ዕድሜው ቢበዛ 75 አመት የሆነ ሰው እንደሆነ የሚደነግግ በመሆኑ፣ በምርጫው ለመወዳደርና ስልጣናቸውን ለማራዘም ሲሉ ህጉን የማሻሻል ሃሳብ ማቅረባቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
የኡጋንዳ ፓርላማ የፕሬዚዳንቱ የዕድሜ ገደብ ይሻሻል በሚለው ሀሳብ ዙሪያ ለመምከር ከዚህ ቀደም በጠራቸው ስብሰባዎች ላይ ከፍተኛ አለመግባባትና ውዝግብ መፈጠሩን ያስታወሰው ቢቢሲ፣ የፓርላማው አባላት በወንበር እየተወራወሩ እስከመፈነካከት ደርሰው እንደነበርም አመልክቷል፡፡
ረቂቅ ሃሳቡ ለፓርላማ ውሳኔ ከቀረበ ቆየት ቢልም፣ በአፋጣኝ ድምጽ ሊሰጥበት ያልቻለው የአገሪቱ ህግ አውጪዎች ውሳኔውን የሚያጸድቅ የድጋፍ ድምጽ ለመስጠት ከሙሴቬኒ መንግስት ለእያንዳንዳቸው 83 ሺህ ዶላር በሙስና መልክ እንዲከፈላቸው በመጠየቃቸው ነው መባሉን ኦልአፍሪካን ኒውስ ዘግቧል፡፡

 ታዋቂው አፕል ኩባንያ ከዚህ ቀደም አምርቶ ለገበያ ካቀረባቸው የተለያዩ ሞዴል የማክ ኮምፒውተሮች ሁሉ ከፍተኛ አቅም የተላበሰውንና በርካታ ስራዎችን የመስራት ብቃት እንዳለው የተነገረለትን አዲሱን ምርቱን፣ አይማክ ፕሮን ከትናንት በስቲያ በይፋ አስመርቋል፡፡
የዓለማችን የወቅቱ የዴስክቶፕ ኮምፒውተር ቴክኖሎጂ ከፍታ ማሳያ እንደሆነ የተነገረለትና ባለ27 ኢንች ስክሪን ያለው አይማክ ፕሮ፤ ምስሎችንና ቪዲዮዎችን በእጅግ ከፍተኛ ጥራት ኤዲት ከማድረግ ባለፈ በፍጥነቱና በሚያከናውናቸው ስራዎች ብዛት አቻ እንደማይገኝለት ተገልጧል፡፡
ከዘራፊዎች ለመከላከል የሚያስችል ራሱን የቻለ ሲስተም ያለውና ማራኪ ገጽታን የተላበሰው አይማክ ፕሮ፤ በምን ያህል  ዋጋ ለገበያ እንደሚቀርብ እስካሁን ድረስ ኩባንያው በይፋ ያስታወቀው ነገር ባይኖርም፣ አንዳንድ መረጃዎች ግን ከ5 ሺህ ዶላር በላይ እንደሚሆን ግምታቸውን መስጠታቸውን ሲኤንቢሲ ዘግቧል፡፡
አይፎን 8፣ አይፎን 8 ፕላስና አይፎን ኤክስ የተባሉትን አዳዲስ እጅግ ዘመናዊ ስማርት ፎን ምርቶቹን በመስከረም ወር ለዓለም ገበያ ያበቃውና በዓለማቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ሽያጭ እያስመዘገበ የሚገኘው አፕል ኩባንያ፤ በአዲሱ የኮምፒውተር ምርቱ ሽያጭ ስኬታማ ይሆናል ተብሎ እንደሚጠበቅም ዘገባው አመልክቷል፡፡


 የመጀመሪያዎቹ 655 መኪኖች በሙሉ ከወዲሁ ተሸጠው አልቀዋል

    ማክላረን እና ቴስላ የተባሉት ታዋቂ የዓለማችን ኩባንያዎች ያመረቷቸው እጅግ ውድ የቤት መኪኖች ዋጋ፣ የአለምን ትኩረት ስበው መሰንበታቸውን  ዘ ቢዝነስ ኢንሳይደር ዘግቧል፡፡
ማክላረን የተባለው ኩባንያ ከለንደን አቅራቢያ በሚገኘው ዋና መስሪያ ቤቱ ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ ይፋ ባደረገው መረጃ፣ ሴና የሚል ስያሜ ለሰጠው የስፖርት መኪናው 1 ሚሊዮን ዶላር የመሸጫ ዋጋ ማውጣቱን ያስታወቀ ሲሆን ለመጀመሪያ ጊዜ ለገበያ ሊያቀርባቸው ያመረታቸውን 500 መኪኖቹን በሙሉ ከወዲሁ ሸጦ መጨረሱን አስታውቋል፡፡
789 የፈረስ ጉልበት አቅም ያለው ሴና፣እጅግ ፈጣንና ምቾት ያለው ልዩ መኪና እንደሆነ ያስታወቀው ኩባንያው፤ የመጀመሪያዎቹን መኪኖቹን በመጪው መጋቢት ወር ጄኔቫ ውስጥ በሚካሄደው አውደ ርዕይ ላይ በይፋ እንደሚያስመርቅ ገልጧል፡፡
ታዋቂው ኩባንያ ቴስላ በበኩሉ፤ በ2019 የፈረንጆች አመት በገበያ ላይ የሚያውለው የመጀመሪያው በኤሌክትሪክ የሚሰራ መኪና የመሸጫ ዋጋው 255 ሺህ ዶላር እንዲሆን መወሰኑን ከሰሞኑ ባወጣው መግለጫ ማስታወቁን ዘ ቢዝነስ ኢንሳይደር ዘግቧል፡፡ ራፒድኢ የሚል መጠሪያ የተሰጠው ይህ እጅግ ዘመናዊ የቤት መኪና፣ በአይነቱ የተለየ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ ኩባንያው ለመጀመሪያ ጊዜ አምርቶ ለገበያ የሚያቀርበውም 155 መኪኖችን ብቻ እንደሚሆን የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ሰሞኑን በሰጡት መግለጫ ማስታወቃቸውን አመልክቷል፡፡ ኩባንያው ገና መኪናዎቹን በማምረት ሂደት ላይ ቢሆንም፣ ለገበያ ሊያቀርባቸው ያቀዳቸውንና እጅግ ውድ የሆኑትን 155 መኪኖቹን በሙሉ ገና ከወዲሁ ለደንበኞቹ ሸጦ መጨረሱን የጠቆመው ዘገባው፤ መኪናዎቹ አንድ ጊዜ ቻርጅ በተደረጉት የኤሌክትሪክ ሃይል እስከ 200 ማይል ርቀት መጓዝ እንደሚችሉም አስረድቷል፡፡ እስከ 1ሺህ የፈረስ ጉልበት የሚደርስ አቅም እንደሚኖረው የተነገረለትን ራፒድኢ በማምረት ላይ የሚገኘው ቴስላ፤ በቅርቡም ሞዴል 3ኤስ የተባሉ የኤሌክትሪክ መኪኖቹን ለመግዛት ከ450 ሺህ ደምበኞቹ የግዢ ጥያቄ እንደቀረበለት ያስታወሰው ዘገባው፤ ኩባንያው የመኪኖቹን ባትሪ በበቂ ሁኔታ ለማምረት ባለመቻሉ 260ዎቹን ብቻ ሊያመርት መቻሉን ጠቁሟል፡፡

ለ75ኛ ጊዜ ለሚከናወነው የ2018 “ጎልደን ግሎብ” ሽልማት በዕጩነት የቀረቡ ፊልሞች ዝርዝር ባለፈው ሰኞ ይፋ የተደረገ ሲሆን  ዘ ሼፕ ኦፍ ዎተር የተሰኘው ፊልም፣ ምርጥ ዳይሬክተርና ምርጥ ሴት ዋና ተዋናይትን ጨምሮ በሰባት ዘርፎች ለሽልማት በመታጨት ቀዳሚነቱን ይዟል፡፡
ስሪ ቢልቦርድስ እና ዘ ፖስት የተሰኙት ፊልሞችም እያንዳንዳቸው በስድስት ዘርፎች ለሽልማት የታጩ ፊልሞች እንደሆኑ የዘገበው ቢቢሲ፤ ሌዲ በርድ የተሰኘው ፊልም በበኩሉ፣ በአራት ዘርፎች በመታጨት ሶስተኛ ደረጃ ላይ መቀመጡን አመልክቷል፡፡
በቴሌቪዥን ተከታታይ ድራማዎች ዘርፍ፣ ለዘንድሮው የ”ጎልደን ግሎብ” ሽልማት ከታጩት መካከል፣ በስድስት የተለያዩ ዘርፎች የታጨው ቢግ ሊትል ላይስ በብዛት በመታጨት ቀዳሚነቱን ይዟል ተብሏል፡፡
የሆሊውድ የውጭ ፕሬስ ማህበር የሚያዘጋጀው አመታዊው የ”ጎልደን ግሎብ” ሽልማት አሰጣጥ ስነስርዓት በመጪው ጥር ወር መጀመሪያ ላይ በቢቨርሊ ሂልስ ካሊፎርኒያ በደማቅ ሁኔታ ይከናወናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡


    ኩራዝ ኢንተርናሽናል አሳታሚ ድርጅት ኦሮምኛ ቃላትን ወደ እንግሊዝኛና አማርኛ የሚተረጉም “ኦዳ” የተሰኘ መዝገበ ቃላት ዛሬ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ ስታዲየም ፊት ለፊት በሚገኘው የኦሮሞ ባህል ማዕከል ያስመርቃል፡፡
በምርቃት ስነ ስርዓቱ ላይ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ኃላፊዎች፣ የመንግስት ባለስልጣናትና ደራሲያን ይገኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ተገልጿል፡፡

 በሩሲያ የሳይንስና የባህል አዳራሽ (ፑሽኪን) በአይነቱ ልዩ የሆነ የሙዚቃ ኮንሰርት ዛሬ ከቀኑ 9፡30 ጀምሮ እንደሚካሄድ ማዕከሉ አስታወቀ፡፡ የሩሲያ ታዋቂ ሙዚቀኞች  ይሳተፉበታል በተባለው በዚህ የሙዚቃ ኮንሰርት ላይ ቫስሊ ፓደለስኒ የተባለው ፒያኖ ተጫዋችና ያና ጋይዱኬቪች የተባለችዋ ቫዮሊን ተጫዋች እንደሚሳተፉ የተገለፀ ሲሆን መግቢያው በነፃ  እንደሆነ ታውቋል፡፡
 በዕለቱ የሩሲያ የሻይ ስነ-ስርዓትና የኮክቴል ግብዣ መሰናዳቱን ገልፀው- ማዕከሉ ሁሉም ሰው በኮንሰርቱ ላይ ተገኝቶ ጥሩ ጊዜ እንዲያሳልፍም ጥሪ አቅርቧል፡፡

 አማኑኤል የአዕምሮ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ከብሬማን ፊልም ፕሮዳክሽን ጋር በመተባበር በአዕምሮ ህመም ላይ ያተኮረና ለማህበሩ ግንዛቤ ያስጨብጣል የተባለ ነጠላ ዜማ ከነገ በስቲያ ሰኞ ከምሽቱ 12፡00 ጀምሮ በሂልተን ሆቴል ይመረቃል፡፡
የአገራችን እውቅ አቀንቃኞችና የሙዚቃ ባለሙያዎች ተሳትፈውበታል የተባለው ነጠላ ዜማ፣ ቪዲዮ የተሰራለት ሲሆን የምርቃት ስነ-ስርዓቱ ታዋቂ ግለሰቦች፣ የሙዚቃ ሰዎች፣ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሀላፊዎችና የህክምና ባለሙያዎች በተገኙበት እንደሚካሄድ ሆስፒታሉ በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡

  ሁለተኛው ምጣት “The second coming” የትኛው “ምጣት” ነው? ዊሊያም በትለር ዬትስ “Things fall apart/the center can not hold/… ያለው ማለቴ ነው፡፡ ሁለተኛው የዓለም ጦርነት አይደለም፡፡ እሱ አልፏል፡፡ … በወቅቱ የነበሩት ሁለተኛው የዓለም ጦርነት የዓለም ፍፃሜ መስሏቸው ነበር፡፡ አሁን እኔ እየተመለከትኩ ካለሁት ዓለም ጋር ሳነፃፅረው፣ ሁለተኛው የዓለም ጦርነት እንደ ፍፃሜ ሳይሆን እንደ መልካም መጀመሪያ ውብና የሚናፈቅ ሆኖ ነው፡፡
በአጭሩ አሁን ያለሁበትን፣ የሚታየኝን ዓለም ልገልፀው ፈለግሁኝ፡፡ መግለፅ መፍጠር ነው፡፡ የዊሊያም በትለር ዬትስ “Second coming” የተፃፈው ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት ቀደም ብሎ ነው፡፡ በቅርብ የተነጣጠረ ራዕይ ሊባል ይችላል፡፡ ሁለተኛውን የዓለም ጦርነት እንደ ክርስቶስ መምጫ አድርጎ ነበር የቆጠረው፡፡ ዊሊያም በትለር ዬትስ “በቅርቡ የዓለም ፍፃሜ ይከሰታል” ለማለት ነበር ግጥሙን የፃፈው፡፡
ዓለም እንደ ግጥሙ በሁለተኛው ዓለም ጦርነት ዳር እስከ ዳር ተንጣለች፡፡ ግን ፍፃሜ ደረጃ አልደረሰችም፡፡ ገጣሚው ራዕዩን ለቅርብና ለሩቅ እንዲሆን አነጣጥሮ ነው የተኮሰው፡፡ ለሰማይና ለጣራ በአንድ ጊዜ አልሞ ነው ግጥሙን ራዕይ አድርጎ የፃፈው፡፡ ጣራው ሁለተኛው የዓለም ጦርነት ሆነ፡፡ ሰማዩ የመጨረሻው የዓለም ፍፃሜ፣ የክርስቶስ መምጫ፣ የቅያማ ቀን … ወዘተ፡፡ የዊሊያም በትለር ዬትስ ግጥም፣ ለአጭር ጊዜና ለመጨረሻውም ጊዜ የሚሰራ ነው፡፡ የመጨረሻው ዘመን በቅርቡ ከመጣ ጣራው ሰማይ ይሆናል፡፡ መጨረሻ መስሎ ማለፊያ የሆነ የሰቆቃ መሸጋገሪያ ከተገኘም ግጥሙ መጨረሻውን ለመጠባበቂያ ይሆናል፡፡
ምናልባት ልዕለ ጥበበኛ “በጥበብ ዘመን ተሻጋሪ ይሆናል” የሚባለው እንዲህ በስራው ውስጥ የረጅምና የአጭር ጊዜ አላማ እያስቀመጠ ስለሚያልፍ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ጥበበኛው ዬትስ በ“second coming” ግጥሙ እጅግ ስኬታማ ሆኗል፡፡ ግጥሙ በሌሎች ከባድ ሚዛን ገጣሚያንና ደራሲያን ተደጋግሞ ተጠቅሷል፡፡ የቺኑዋ አቼቤ “Things fall apart” የሚለው የአንዱ ድርሰት ስራው አርዕስት በዚሁ “የሁለተኛ ምጣት” ግጥም አንጓ የተቀነጠሰ ነው፡፡
እርግጥ እኔ ገጣሚ አይደለሁም፡፡ ግን ፎርሙላው ገብቶኛል፡፡ ወደፊት የሚከሰተውን ለማወቅ እንደ ታሪክ አዋቂዎች የቀድሞውን ታሪክ ማጥናት አያስፈልገኝም፡፡ ከኋለኛው ታሪክ አንድ ነጥብ ብቻ እይዛለሁኝ፡፡ ወደ ኋላ ያለው ታሪክ “መጀመሪያ” አለው፡፡ ይኼ ነጥብ በቂ ነው፡፡ የኋለኛው ታሪክ መጀመሪያ እንዳለው ሁሉ … መጪው ታሪክ ደግሞ “መጨረሻ” አለው፡፡ ይኼንን የሚያውቅ ሁሉ ባለ ራዕይ ነው፡፡ የተጀመረው ነገር መጠናቀቁ አይቀርም፡፡ መጠናቀቁ እንደማይቀር በደመነፍስ ሳይሆን በሳይንስም ሆነ በፍልስፍና ሜታፊዚካል መጠይቅ መልክ ተጠቅመን ብንመረምር የምንደርሰው አንድ ነጥብ ላይ ነው፡፡ የተጀመረ ነገር ሁሉ መጠናቀቁ … በዚህም ተባለ በዛ አይቀርም፡፡
ምናልባት ልዩነትና የሀሳብ ግጭት ሊነሳ የሚችለው ከዚህ ጥልቅ ስምምነት ወደ ተናጠልና “specific” ጉዳዮች ስንመጣ ነው፡፡ ለምሳሌ መጨረሻው መቼ ነው በእርግጥ የሚሆነው? … ያወዛግባል፡፡ ከጊዜ ጋር የ “ሳቢያ ወይንም መንስኤ” ጉዳይ ይመጣል፡፡  በምን ምክኒያት ነው መጨረሻው በተባለው (መቼ) ላይ የሚያርፈው፡፡ በግርድፉ ነጥብ፤ ማለትም “የተጀመረ ነገር መጠናቀቁ አይቀርም” የሚለውን በተመለከተ ሁላችንም ባለ ራዕይ ነን፡፡ ልዩ ባለ ራዕዮች የሚያስፈልጉት የጊዜና ቦታ፣ የሳቢያና መንስኤን … ትንንሽ ጥያቄዎች እንዲመልሱልን ብቻ ነው፡፡ ትልቁን እውነት ሁላችንም እናውቀዋለን፡፡ ጥቅሉን እውነት በማወቅ ረገድ ሁላችንም አንድ አይነት ነን፡፡ ልዩነት የሚመጣው በትንንሾቹ ጥያቄዎች ላይ ነው፡፡
በአእምሮአችን የሚመጡ ሀይማኖታዊም ሆኑ ዓለማዊ ባለ ራዕዮች ወይንም ትንቢት ተናጋሪዎች ትንንሹን ጥያቄ ለመመለስ የቻሉ ናቸው፡፡ ግን ትንንሾቹን ጉዳዮች በደንብ ቢተነብዩም ስለ መጨረሻው ግን የሰጡት ትንበያ ትክክል መሆኑ የሚታወቀው ፍፃሜው ላይ ነው፡፡
ባለ ራዕይ ማለት፤ መጨረሻውን በቅርብና በሩቅ በሁለቱም አንፃር ገፍቶ ጥሩ ግምት ማስቀመጥ የቻለ ማለት ነው ለኔ፡፡ ዊሊያም በትለር ዬትስ ይሄን ነው በግጥም ያደረገው፡፡ ምጣት አንድ ሆኖ እንደማይቀር ገብቶታል፡፡ እሱ ብቻ ሳይሆን ሁላችንም ይገባናል፡፡ ሁላችንም ባይገባን ኖሮ ግጥሙም በተለያዩ የፍፃሜ አደጋ ሞዴሎች ላይ እየለዋወጥን ባልሞከርን … ግጥሙም ተራ ሆኖ በተረሳ ነበር፡፡
ግን ዊሊያም በትለር ዬትስ እኛ የምንፈራውን የሚፈራ፣ እኛ የምናውቀውን የሚያውቅ ገጣሚ ነው፡፡ እኛ የምንፈራው ፍፃሜውን ነው፤ እኛ የምናውቀው መጨረሻው እንደማይቀር ነው፡፡ አንዴ መጥቶ፣ የመጣበትን ግብ ሳይፈፅም የሄደ ጥፋት ተመልሶ መምጣቱ እንደማይቀር እንሰጋለን፡፡ ስጋታችን ከምናውቀው ነገር የመነጨ ነው፡፡ እውቀታችን ለሁላችንም አንድ ነው፡፡
ክርክሩ ያለው የጊዜና ሳቢያ መንስኤ ላይ እንጂ መምጣቱ የማይቀረው መጨረሻ “እንደወጣ እንደማይቀር” እናውቃለን፡፡ ክርክሩ ያለው “ጊዜው አልደረሰም” እና “ጊዜው ደርሷል” በሚሉ ገማቾች ላይ ነው፡፡ አሁን ባይደርስም መድረሱ ግን እንደማይቀር ሁሉም ያውቃል፡፡
ገጣሚ፣ ጥበበኛ ጥበቡን ዘላለማዊ ለማድረግ ካለው ፍላጎት የተነሳ እሱም ከጊዜ ጋር ጠበኛ ነው፡፡ ሀይማኖተኞች ወይንም ትንቢተኞች (ሳይንስም የትንቢተኛ አይነት ነው፤ የትንበያ ዘዬው ቢለያይም) “ጊዜው አልደረሰም/ደርሷል” ነው የሚያከራክራቸው፡፡ ለቅርብም የሚሆን ዜማ ይፈበርካል፡፡ ቅርበትና ርቀት መሀል ያለውን የጊዜ ትርጉም የሚዋጅ ግጥም ከተፈበረከ ጊዜ ከጥቅም ውጭ ይሆናል፡፡ ወይንም በገጣሚ ሰለሞን ደሬሳ አገላለፅ፡- “የጊዜ ቋንጃ ተበጥሷል፡፡” “የት ይደርሳል የተባለ ጥጃ ልኳንዳ ቤት ቀረ” የሚል የመዘባበቻ ሀረግ አብዝተን ስንጠቅስ እንደመጣለን፡፡ ጥጃውን መመሰል የተፈለገው በሰው ልጅ ነው፡፡ እንጂማ ጥጃ የት ይደርሳል፣ ከልኳንዳ ቤቱ ውጭ? …
ግን እቺ የጥጃ አባባል የቅርቡን ራዕይ የምትገልፅ ትመስለኛለች፡፡ የሰው ልጅ ስንት ጠፈር ቧጥጦ፣ ስንት ተአምር ይፈጥራል ሲባል፣ በሁለተኛው አለም ጦርነት ኒዩክለር ቦንብ እርስ በራሱ እጣ ተጣጥሎ ድምጥማጡ ጠፋ … እንደ ማለት ሊታይ ይችላል፡፡ ግን የፈለገ ጠፈር ቢቧጥጥም “በስተመጨረሻ እህሳ?!” ከተባለ፣ ያው ፍፃሜው ጋር ደረሰ ነው መልሱ፡፡ የጥጃውም መጨረሻ ልኳንዳ ቤቱ፣ የሰውም ፍፃሜ ሞቱ ነው፡፡ አሰቃቂ ወይንም ሰላማዊ ብለን ሞቱ የቀረበበትን ሁኔታ ብንገልፀውም በመጨረሻው ሞቱ ነው፡፡ መጨረሻው ይህ መሆኑን ሁሉም ያውቃል፡፡ የት ይደርሳል የተባለ! እያለ ይዘባበታል፡፡ ህይወቱን በተለያየ ሰው ሰራሽ ትርጉሙ ቅርፅ አንፆ፣ መጨረሻውን የረሳ ይመስላል፡፡ አንድ ባለ ራዕይ በገጣሚ ወይንም በትንቢት ተናጋሪ መልክ ተነስቶ ስለማይቀረው ነገር ሲያስታውሰው ይደነግጣል፡፡ የመደንገጥና የማስደንገጥ ሚና ለራሳቸው በይነው የሚንቀሳቀሱ ሰዎች አሉ፡፡ አስደንጋጮቹ “ጊዜ ደርሷል!” የሚሉት ናቸው፡፡ “ወይኔ ኖሬ ሳልጠግብ፣ መሞት ሳልለማመድበት” ብለው የሚደነግጡትን የሚያስጥሉ አላጋጭ ነን የሚሉ ይነሳሉ - “የዓለም ፍፃሜ ደርሷል” የሚሉት ውሸት ነው … ፀሐይ ተነፋፍታ እስክትፈነዳ 20 ቢሊዮን አመት ገና ይፈጃል ይላሉ፡፡
ካርል ፓፐር የሚባል በሳይንስ ላይ ጥሩ አድርጎ በመፈላሰፉ የሚከበር ሰው፣ ስለ ትንቢት የሚለው ነገር እኔ ከምለው ጋር በጣም ልዩነት እንዳለው መጠቆም እፈልጋለሁኝ፡፡ ፓፐር በመሰረቱ ትንቢትና ሳይንስ ሁለት በተለያዩ ቋንቋ የሚያወሩ፣ አንዱን ቋንቋ ወደ ሌላው መቀየር የማይቻል፣ የተለያዩ አለማት ፍጥረት ናቸው ይላል፡፡ ወይንም እንደማለት ይቃጣዋል፡፡
እሱ ትንቢትን እምነት በሚል መጠቅለያ ነው የሚጠራው፡፡ እምነት ማለት እኔ ከላይ ስፅፍ የመጣሁትን ሁሉ ሳያጓድል ይላል፡፡ ሀይማኖት ግን እኔ ስል ከመጣሁት በተጨማሪ ከማይቀረው መጨረሻ ማስጣያ መፍትሄው እኔው ዘንድ ነው ይላል፡፡ በዓለም ላይ የገነኑ ሀይማኖተኞች በተለይ ከክርስትና በኋላ ያሉት ይሄንን ነው የሚሉት፡፡ የማስጣያ መፍትሄው ሁሉም ሀይማኖቶች ጋር ሳይሆን “እኔ ብቻ” ጋር ነው የሚለው ያስማማቸዋል፡፡ … ለሁሉም የማይቀረው መጨረሻ “ከእኔ ብቻ ጋር ከሆንክ” ለአንተና እኔ የመጨረሻው መጀመሪያ ይሆንልናል…፡፡ ሁሉም በተናጠል … በእየ ዘውጋቸው ሆነው ይሄንን ይላሉ፡፡ ያሉትን ለማሳመን ይጥራሉ፡፡
ካርል ፓፐር “ትንቢት ወይም ሀይማኖት ሊመረመር (verify ሊደረግ) ስለማይችል ውሸት መሆኑንና ማረጋገጥ፣ ወይንም መፈተን አይቻልም” ይላል፡፡ በካርል ፓፐር ፍልስፍና፤ ዋነኛውና እና ቁልፉ ነገር “falsifibility” ነው፡፡ “አንድን ሀሳብ ወይንም ኩነት ውሸት መሆኑን ማረጋገጥ በሚያስችል ደረጃ ሊፈተን የሚችልበት ክፍተት ከሌለው … ይሄ ነገር ሃይማኖት ነው” ይላል፡፡ ይቀጥልናም፤ “ሁሉም “ሳይንስ” … ውሸት መሆኑን የሚያሳይ ክርክርን የማስተናገድና በቤተ ሙከራ የመፈተን ክፍት አቋም አለው” ይላል፡፡
በዚህ ሀሊዮት አንፃር እኔ እየፃፍኩ የመጣሁትን ምልከታዬን አጉልተን ስንመለከተው፣ ትንቢት እንጂ ሳይንስ እያወራሁ እንዳልሆነ ወዲያው ግልፅ ይሆንልናል፡፡ እኔ ከመነሻው እንደ ሚስማር እየደጋገምኩ ስቀጠቅጠው የነበረ አረፍተ ነገር ነበር፡፡ ይኼ አረፍተ ነገር “መጀመሪያው እንዳለ ሁሉ መጨረሻው መኖሩ አይቀርም” የሚል ነው፡፡ መጨረሻው ስለመኖሩ ከእምነት ውጭ ፍፃሜውን አቅርቦ በማሳያ መነፅር አስጠግተን ማጥናት ስለማንችል፣ ይህ አረፍተ ነገርን በሳይንሳዊ መንገድ “falsify” ማድረግ አንችልም፡፡ በሳይንሳዊ መንገድ ሊመረመሩና መረጃ ሊቀርብባቸው የማይችሉ ድምዳሜዎች ሁሉ በ“ሃይማኖት” ወይ “እምነት” ዘውግ ስር ለካርል ፓፐር የሚካተቱ ናቸው፡፡ … በሳይንስ ተመርምረው የእውነት (fact) እና የውሸት (belief) መጠናቸው ሊታወቅ (verify ሊደረግ) አይችልም፡፡ ስለማይችል አይመረመሩም፡፡ ስለማይመረመሩ ሃይማኖት ናቸው፡፡ ሃይማኖት ከትንቢት ንጥረ ነገር የሚሰራ ርዕዮተ ዓለም (world view) ነው፡፡ ሳይንስ ደግሞ ከተጨባጭ መረጃ፡፡