Administrator

Administrator

 ለኢየሩሳሌም የእስራኤል መዲናነት እውቅና በመስጠታቸው የደረሰባቸውን ዓለማቀፍ ውግዘት ተከትሎ፣ “ብዙ እየረዳኋት አታከብረኝም” በሚል ለፍልስጤም የሚሰጡትን እርዳታ እንደሚቀንሱ ሲዝቱ የነበሩት ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ እንዳሉትም፣ ለፍልስጤም ስደተኞች ይሰጡት ከነበረው እርዳታ ላይ ከግማሽ በላይ መቀነሳቸው ተዘግቧል፡፡
አሜሪካ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት በኩል ለፍልስጤም ስደተኞች ስትሰጠው ከነበረው 125 ሚሊዮን ዶላር እርዳታ ከግማሽ በላይ የሚሆነውን ወይም 65 ሚሊዮን ዶላሩን መቀነሷን በይፋ ማስታወቋን የዘገበው ዘ ኢንዲፔንደንት፤ ይህን ተከትሎም በዌስት ባንክ፣ ጋዛ ሰርጥ፣ ሊባኖስ፣ ዮርዳኖስና ሶርያ የሚገኙ ፍልስጤማውያን ስደተኞች ህልውና ከፍተኛ አደጋ ላይ ይወድቃሉ የሚል ስጋት መፈጠሩን አመልክቷል፡፡
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ፣ አገራቸው ይህንን ውሳኔ ያስተላለፈቺው ማንንም ለመበቀልና ለማጥቃት በማሰብ ሳይሆን፣ ገንዘቡን ከመለገሳችን በፊት በተመድ ስር የሚገኘውን የእርዳታ ተቋም አጠቃላይ አሰራር በጥንቃቄ መፈተሽ በማስፈለጉ ነው ብለዋል፡፡ ተቋሙ ለፍልስጤም ታጣቂዎች ድጋፍ በማድረግና አድልኦአዊ አሰራር በመከተል በእስራኤል ተደጋጋሚ ትችት ሲሰነዘርበት እንደቆየ ያስታወሰው ዘገባው፤የትራምፕ አስተዳደር በተቋሙ አሰራር ላይ ፍተሻ ለማድረግ መወሰኑም ከዚህ ጋር ግንኙነት ሊኖረው እንደሚችል እየተነገረ ነው ብሏል፡፡
በተያያዘ ዜና፣ ከሰሞኑ አፍሪካውያንን በአደባባይ ዘልፈዋል በሚል ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሳይቀር ከፍተኛ ውግዘት የገጠማቸውና በብዙዎች ዘንድ በአእምሮ ጤና ችግር ሲታሙ በቆዩት ዶናልድ ትራምፕ ላይ ምርመራ ሲያደርጉ የቆዩት የዋይት ሃውሱ ሃኪም፣ ማክሰኞ ዕለት በሰጡት መግለጫ፤ ትራምፕ በአእምሮም ሆነ በአጠቃላይ ጤንነታቸው ቅንጣት ታህል ችግር የሌለባቸው ጤነኛ ሰው መሆናቸውን አረጋግጫለሁ ብለዋል፡፡
ከምርጫ ቅስቀሳቸው ጊዜ አንስቶ በሚናገሯቸው አጉል ንግግሮችና በሚወስዷቸው አስደንጋጭ ውሳኔዎች አለም በወፈፌነት ሲጠረጥራቸው የቆዩት ትራምፕ፤ ሌሎች ምርመራዎችን ለሚያደርግላቸው ሃኪም “እባክህን የአእምሮዬንና የአስተሳሰብ ሁኔታዬንም አብረህ መርምረኝ” የሚል ጥያቄ ማቅረባቸውን የዘገበው ሮይተርስ፤በዚህ መሰረት በተደረገው ምርመራ ሙሉ ጤናማ መሆናቸው መረጋገጡን ገልጧል፡፡ የአእምሮ ብቃታቸው አገር ለመምራት የሚያስችልና ትክክለኛው ደረጃ ላይ ነው የተባለላቸው ትራምፕ፣ አጠቃላይ ጤንነታቸው በጥሩ ደረጃ ላይ ቢገኝም፣ እንቅስቃሴ ማድረግና ከ10 እስከ 15 ፓውንድ ክብደት መቀነስ እንደሚገባቸው በሀኪማቸው መመከራቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡

በሳይቤሪያ በምትገኘው ኦይማይኮን የተባለች የገጠር መንደር ውስጥ በሳምንቱ መጀመሪያ ከዜሮ በታች ኔጌቴቭ 62 ዲግሪ ሴንትግሬድ የደረሰ ሃይለኛ ቅዝቃዜ የተመዘገበ ሲሆን ቅዝቃዜው በመንደሯ የነበረውን የሙቀት መለኪያ መሳሪያ በመስበር ከጥቅም ውጭ ማድረጉ ተነግሯል፡፡
እ.ኤ.አ በ1993 ከዜሮ በታች 67.7 ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ ሃይለኛ ቅዝቃዜ የተመዘገበባት መንደሯ፤500 ያህል ቋሚ ነዋሪዎች እንደሚገኙባትና ከፍተኛ የቱሪስት ፍሰት ያላት መሆኗን የጠቆመው ዘገባው፣ ነዋሪዎች ቅዝቃዜውን ለመቋቋም ተቸግረው እንጨትና ከሰል በማቀጣጠል ህይወታቸውን ለማትረፍ ደፋ ቀና እያሉ እንደሚገኙ አመልክቷል፡፡
በአለማችን ታሪክ ዝቅተኛው የሙቀት መጠን ሆኖ የተመዘገበው በምስራቃዊ አንታርክቲካ እ.ኤ.አ በ2013 የተከሰተው ከዜሮ በታች ኔጋቲቭ 94.7 ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ ቅዝቃዜ እንደነበር ዘገባው አስታውሷል፡፡

   ሹዋን ቮኬሽናል ኮሌጅ  ኦፍ ካልቸር ኤንድ ኮሙኒኬሽን የተባለው የቻይና ኮሌጅ ተማሪዎች ሰሞኑን በወሰዱት የሴሚስቴር ማጠቃለያ ፈተና ላይ የመምህራቸውን ስም እንዲጽፉ የሚያዝዝ አንድ ጥያቄ ቀርቦላቸዋል፡፡
ቤጂንግ ታይም እንደዘገበው፤ተማሪዎቹ የሰባት ሰዎችን ፎቶግራፍ የያዘ የጥያቄ ወረቀት የቀረበላቸው ሲሆን ከሰባቱ መካከል መምህራቸውን መርጠው ከስሩ ስሙን እንዲጽፉ ተጠይቀዋል። ጥያቄውን በትክክል የመለሱት ተጨማሪ ማርክ ባይሰጣቸውም፣ የተሳሳቱና መምህራቸውን ወይም ስሙን መለየት ያልቻሉት ግን ካገኙት ውጤት ላይ 41 ነጥቦች ተቀንሶባቸዋል፡፡
በኮሌጁ የሚያስተምሩት ሁ ቴንግ እንደሚሉት፤ በአይነቱ የመጀመሪያው የሆነውን ይህን ጥያቄ በፈተናው ውስጥ ማካተት ያስፈለገው፣ ተማሪዎች ከመደበኛ ትምህርታቸው ባሻገር በዙሪያቸው ላለው ነገር ምን ያህል ትኩረት እንደሚሰጡ ለመገምገም በሚል ነው፡፡ ይህ የኮሌጅ ፈተና ጥያቄ በቻይናውያን ማህበራዊ ድረገጾች መነጋገሪያ ጉዳይ ሆኖ መሰንበቱን የጠቆመው ዘገባው፣ አንዳንዶች ክፉኛ ቢያብጠለጥሉትም የተወሰኑት ግን የመምህርን ስም ማወቅ ግዴታ ነው ሲሉ ድጋፋቸውን እንደሰጡት አመልክቷል፡፡

Saturday, 20 January 2018 12:31

የእግዜር ስላቅ

ነገ እኩለ-ቀን ላይ
ምሳ አብረን ልንበላ ተቃጥረን ነበረ
ጓዴን ዛሬ ማታ
ከቀጠሮው በፊት ሞት ቀድሞት አደረ
ይህ ገብቶት ነው ለካ
እኛ ስንቃጠር እግዜር ከላይ ሆኖ ሲስቅ የነበረ፡፡

ፈሪሃ እግዚአብሔር
‹እግዚአብሔርን ፍራ› እያለ ሲሰብከኝ በነጋ በጠባ    እግዜርን ፈርቼ
እግዜርን ሸሽቼ
ደብር መሄድ አቆምኩ ገነት እንድገባ፡፡

መልክኣ ሰብእ
አውቃለሁ ኃጢአቴን ብዙ በድያለሁ
ቃልህን ገድፌ ሺ ጊዜ ስቻለሁ፤
ቢሆንም ቢሆንም
ንስሀ ለመግባት ስለማይሆንልኝ
አቤቱ ጌታ ሆይ ና ተሰቀልልኝ!
(“አገሬን ሰቀሏት” ከተሰኘው የገጣሚ
ደሱ ፍቅር የግጥም መድበል የተወሰደ)

Saturday, 20 January 2018 12:18

የወቅቱ ጥቅስ

“ያልተደራጀ ኃይል፤ ኃይል አይደለም!”
     የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ

Saturday, 20 January 2018 12:26

ማራኪ አንቀፅ

 አንድ የአሜሪካን ባህር ኃይል አባል ታሪክ ትውስ አለው፡፡ አንድ ጦር መርከብ ከአንድ ወደብ ተነስቶ ወደ ሌላ ግዳጅ በሚሰማራበት ወቅት የእያንዳንዱ ክፍል ኃላፊ ያለውን የሰው ኃይልና የተመደበበትን ክፍል ምን ያህል ዝግጁ ሆኖ እንደሚሰለፍ ለካፒቴኑ እየመጣ ተራ በተራ ሪፖርት ያደርጋል፡፡ በአንደኛው ግዳጅ ላይ ቀዘፋው ተጀምሮ አንዱ መርከበኛ የደረሰበት ጠፋ፡፡ የመርከቧ ጓዳ ጎድጓዳ ሁሉ ተፈለገ፡፡ አልተገኘም፡፡ ይህንን አሳዛኝ ዜና ለባህር ኃይል መደብ ሪፖርት አድርገው ወደ ፊት ቀዘፋቸውን አቀኑ፡፡
ይህ ልጅ በጠፋበት አካባቢ አንድ ሰማያዊ ዓሣ ነባሪ በዓሣ አጥማጆች ተሰገረ፡፡ ዓሣ ነባሪውን ያሰገረችው መርከብ፣ የራሷ ቄራ ነበራትና ዓሣ ነባሪውን ጎትታ ወደ ቄራው እገባችው፡፡ በላቾቹ በፍጥነት የዓሣ ነባሪውን ሆድቃ አንዳች በሚያክለው ቢላቸው ሲበረግዱ፤ አንዱ ጥግ ላይ ያ ከመርከብ ላይ ጠፋ የተባለ መርበኛ እጥፍጥፍ ብሎ እንቅልፉን እየለጠጠ ነበር፡፡ በላቾቹ ተደናግጠው ሲቀሰቅሱት፤ “ምነው የዘብ ሰዓት ደረሰ እንዴ?” ብሎ መጠየቁ ይወራለታል፡፡
ይህ መርከበኛ ከመርከቧ ላይ እንደወደቀ ዓሣ ነባሪው ዋጥ አድርጎታል፤ ሳያውቀው ወደ ሞቱ እያዘገመ ነበር፡፡ ዛሬ ዕድሜ ለዓሣ አስጋሪዎች በሕይወት ተረፈ፡፡ ይሁን እንጂ ሕይወቱን በሙሉ ለምጣም ሆኖ ኖረ፡፡
“የእኛስ ምን ይሆን ዕጣችን?...” አውጠነጠነ፡፡ ምላሽ የለውም፡፡ መፍጠን አለበት፡፡ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት የሻርክ ራት ሆነው የቀሩ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ አሜሪካውያን፣ ጀርመናውያንና እንግሊዛውያን መርከበኞች ታሰቡትና አሁን ሲሆን ያየ ይመስል ዘግንኖት አይኖቹን ጨፈነ። ደገመና “የእኛስ መጨረሻ ምን ይሆን?” ሲል በረጅሙ ተነፈሰ፡፡ በእንዲህ ዓይነቱ ዓለም ውስጥ ሲኖር መግቢያው ብቻ ሳይሆን መውጫውንም ማውጠንጠን የግድ ነው፡፡
ጀርባዋ ላይ በእርዳታ የታደለ ቦክራ የዱቄት ወተት አለ፡፡ ብዙዎቹ መርከበኞች በጥብጦ የመጠጣት ልምድ የላቸውም፡፡ ያሬድ ሐጎስ ባህር ኃይል በልክ ሰፍሮ የሚሰጠው ምግብ ከአንጀቱ ጠብ ስለማይል ቦክራውን በጥብጦ በመጠጣት የምግብ ፍላጎቱን ያሟላል፡፡ ከተማ ወጥቶ ተዝናንቶ እስኪመለስ የበጠበጠውን የቦክራ ወተት ፍሪጅ ውስጥ አስቀምጦ ይሄዳል። ምሽቱ ሲጋመስ በደንብ ቀዝቅዞ ስለሚጠብቀው አንጀት አርስ እንደሚሆንለት ዕምነቱ ነው፡፡ ይህንን አልሞ በጥብጦ የማስቀመጥ ባህሉን ቢያዳብርም፣ በቅርቡ ግን ማንነቱን ያላወቀው መርከበኛ እየሰረቀ ጠጥቶበት በተደጋጋሚ ባዶ ጆግ ፍሪጅ ውስጥ አጋጥሞታል፡፡ ይህን ቀበኛውን ለማጥመድ ዛሬ ቦክራው ውስጥ “ፈንጂ” አጥምዶበት ነው ፍሪጁ ውስጥ ያኖረው፡፡
(ከደራሲ ዘነበ ወላ “መልህቅ”
የተሰኘ አዲስ መፅሐፍ ላይ የተቀነጨበ)

Saturday, 20 January 2018 12:23

“ሀ ያሉ ጦም አደሩ!” (ወግ)

     እኔና ቤቴ ግን እግዚአብሔርን እናመሰግናለን! ማግኘት ምንድን ነው? ምስጋና የሚሰጠውስ ለየትኛዉ ዓይነት ማግኘት ነው? መልሱ ምንም ሆነ ምን እኔና ቤቴ ግን ተርፎን ስለምንረጨዉ ንዋይ ሳይሆን፤ ያዘነልን ስለሚወረውርልን፤ የራራ ስለሚያበድረን ወር መፍጃ እናመሰግናለን፡፡
አንዳንዴ ትካዜዬ ሌላ ትካዜን ይወልድና በሣሣዉ ኑሮዬ ላይ ተንጠላጥዬ፣ የወሩ አራት ሳምንታት በሠሩት መስኮት አጨነቁራለሁ። መስቀልያ ሠርቶ በጊዜ አናት ላይ በቆመው ወር ላይ እኔን የመሰለ አንድ የመንግስት ድርጅት ተቀጣሪ፣ በአራት ሚስማሮች ተቸንክሮ ይታየኛል። ሚስማሮቹ የወሩን አራቱን ሳምንታት ይወክላሉ፡፡ ይህን ተቀጣሪ ስለማቀው መልስ፤ በጥያቄ ወጥሬ እይዘዋለሁ፡፡ ያለመሰልቸት የማውቀዉን መልስ ይመልስልኛል፡፡ ገነት እንደገባው ወንበዴ ንጹሕ ልብ አለው፡፡ ደጋግሞ እንደሚናገረው፤ ተቀጣሪው በመማሬና ሥራ በመያዜ አተረፍኩ የሚለው ወር ሲደርስ ማግኘት፣ ወሩ ከደረሰ በኋላ ማጣትና ወሩ እስኪደርስ መበደርን ነው፡፡
በሌላ ጊዜ ደግሞ ትካዜዬ ሌላ ትካዜን ወልዶ፣ የወሩ አራት ሳምንታት በሠሩት መስኮት ሳጮልቅ፤ እኔን የሚመስለው ተቀጣሪ በመስቀሉ ላይ እንዳለ፣ እንደ ንፋስ የቀለለ እንጀራ እየቆረሰ፤ ልጅ እያለ ለእንቁጣጣሽ አበባ ይስልበት ከነበረዉ የአስር ሳንቲም ቀለም በቀጠነ ወጥ እያጠቀሰ፤ ባልጠረቃው ሆዱ ዉስጥ እንዲህ ያስባል፡-
‹‹የተማረና ሥራ ያለው ሰውን ከሌላው (ከሌለው) የሚለየው ምንድነው? እውነት የሚኖረዉ የተደላደለ ህይወት ወይስ እንደ መስቀል ከጫንቃው የተሸከመው መከራ? እውነት ይህን ኑሮ፤ ኑሮ ካሉት መቃብር ይደላል፡፡ የተማረና ሥራ ያገኘ ሰው የሚያመሰግነዉ ስለሚኖረዉ መልካም ህይወት ሳይሆን፣ አምኖ የሚያበድረው በማግኘቱ ነዉ፡፡ በዚህ ዘመን ገንዘብ የሚሰጥ አበዳሪ ማግኘት፤ ንስሃ የሚሰጥ አባት ከማግኘት የተሻለ ጥሩ ስሜትን ይፈጥራል፡፡›› እንዲህ እንዲህ እያለ በሚጎርሰው የሣሣ እንጀራ ልክ፤ የሣሣ ቅኔ ይቀኛል፡፡
የቸገረዉ ተኝቶም አያርፍም፡፡ እኔም ተምሬ ሥራ ከያዝኩ ጀምሮ አርፌ አላውቅም፡፡ ከቸገረው መሀል የደላዉ በቁሙ እከክ ወርሶ እንዳይጨርሰው ቅቤ ሲጋት ያድራል፡፡ የፈረደበት ወተቱን ቅቤ ሊያደርግ ሲንጥ ያድራል፡፡ በጣም የፈረደበት ደግሞ ወተት ሊያመርት በሬ ሲያልብ ያነጋል፡፡ በድቅድቁ ጨለማ መስቀልያ ሠርቶ በጊዜ አናት ላይ በቆመው ወር ላይ በአራት ሚስማር ተቸንክሮ የተሰቀለው ተቀጣሪ ደጋግሞ ሲጮህ ይሰማኛል፡-
‹‹አቤቱ የምሠራውን አላውቀውምና ይቅር በለኝ››፡፡
ተቀጣሪውን ከመስቀሉ ጋር አብረው የሠፉት አራቱን ሳምንታት የሚወክሉ አራቱ ሚስማሮች ዘወረደ፣ ቅድስት፣ ኒቆዲሞስ እና ሆሳህና ይባላሉ። የጊዜ ዉጤቶች በመሆናቸው፣ ሳምንታቱ ተራ በተራ ወቅታቸውን ጠብቀው ይስሙታል ወይ ይሰሙታል፡፡
አራት ሳምንታት - ከጊዜ ምንጭ እየወረዱ ሰባት፣ ሰባት ቀናትን በእንስራቸው  እየጨለፉ ተሸክመው የሚመጡ-የማይደክማቸው፣ የማይሰለቻቸው ወረተኞች (ደከመው፣ አልደከመው ጊዜ እንደው ወረተኛ ነዉ)፡፡ አራት ሳምንታት-እንደ መድኃኒተኛ ደስታንና ሀዘንን ሲያሻቸው ለየቅል፣ ካልመሰላቸውም በርዘው መፍጠር የሚችሉ። አራት ሳምንታት-በጭፍግና በኢ-ጭፍጋቸዉ የፊት ገጽታን የሚቆጣጠሩ፤ የፊት ቆዳን ወደ ጎን በመለጠጥ አልያም ወደ ላይ በመቆልመም የተካኑ፡፡ አራት ሳምንታት- አራት የእርግዝና ሳምንታት፡፡ እልፍ ምኞት ተረግዞ፤ እልፍ ደስታና ሀዘን የሚወለድባቸዉ፡፡ የተረገዙት ጨንግፈው፤ የተወለዱት የማይበረክቱባቸው፡፡
እነዚህ አራት ሳምንታት ባላሰበበት እየዋለ፤ ባልዋለበት እያደረ የሚኖረዉ አዲሳባዊ መንግሥት መሥርያ ቤት ተቀጣሪ ኑሮ፤ ፈትሎ የሚያዉለበልባቸዉ ወርሃዊ ሰንደቅ-ዓልማዎች ናቸዉ፡፡ ከአራቱ አቅጣጫ የሚፈልቁት ነፋሳት የሰንደቅ-ዓልማዉ አጫፋሪዎች እና አስጨፋሪዎች ናቸዉ፡፡ እነዚህ አራት ሳምንታት ከቀኝ ከግራ፤ ከፊት ከኋላ ተደግነዉ ተቀጣሪዉ እንደፈረስ ሠርክ ዳንግላሳ እንዲጫወታቸዉ የሚጋርዱ ድግምቶች ናቸዉ፡፡ ግን እነዚህን ድግምት ማነው ያሠራቸው?...ማነዉ የሠራቸው? ...ማነዉ ያሠራብን? ...ለምን ጉዳይ? ...ቀጣሪ እንጂ ተቀጣሪ እንዳያልፍለት ነው? ሚስማራቱስ ስለ ምን አራት ሆኑ? ትርጉማቸውስ?

ዘወረደ
የመጀመርያዉ ሚስማር፡፡ ከደሞዝ በፊት ያለ ሳምንት፡፡ ጨለማዉ ሲጠልቅ ጎህ ሲቀድ ታየ፡፡ ‹ፔይ ሮል› ከአካውንታንቶች ወደ አጽዳቂዎች ወረደ፡፡ ገንዘብ ከከፋዮች አካውንት ወደ ተከፋዮች አካውንት ተወረወረ፡፡ የተቀጣሪዎች ኪስ ገንዘብ ሊጠነሰስበት ይሟሽ፣ ይታጠን ጀመረ፡፡ ደሞዝ መድረሱን የተረዱና ደህንነት የተሰማቸው አበዳሪዎች እጃቸዉ ይፈታ ጀመር፡፡ ደሞዝ ቀድመው የተቀበሉ የሌላ ድርጅት ተቀጣሪዎች /ከአበዳሪዎች የአንበሳዉን ድርሻ የሚይዙት/ እየጋበዙ ያበድሩ ገቡ፡፡ ችግሩ ብድሩ እንደሚከፈላቸው እያወቁ እንኳን ማስጠንቀቅ ያበዛሉ፡፡ በዚህ ሳምንት ተቀጣሪ የደረሰ ደሞዙን ተማምኖ በወሩ ከተበደረው ገንዘብ ድምር የሚልቅ ገንዘብ ይበደራል፡፡
በዘወረደ ቀጣሪዎችና በድርጅቶችና በተቋማት ‹ፒቲ ካሽ› ቀናቸውን የሚገፉ አካዉንታንት፣ ሌላዉ ተቀጣሪ ደሞዝ በወቅቱ እንዳይከፈለው የሚያደርጉት ያላሰለሰ ጥረት እልባት አግኝቶ ደሞዝ ወደ ባንክ ይወርዳል፡፡ የብር መቁጠርያ ጣት ማራሻ ስፖንጆች በውሃ ይርሳሉ፡፡ መስቀልያ ሠርቶ በጊዜ አናት ላይ በቆመዉ ወር ላይ በአራት ሚስማር ተቸንክሮ ያለው ተቀጣሪ ግን አሁንም ደጋግሞ ይጮሀል፡-
‹‹አቤቱ የምሠራውን አላውቀውምና ይቅር በለኝ››፡፡  
ቅድስት
ሁለተኛው ሚስማር፡፡ የመልካሞች መልካም! በመንግሥት መሥርያ ቤቶች ከልደታ እስከ ባዕታ የሚባለው በሌሎች ደግሞ ከደሞዝ በኋላ ያለው ሳምንት ነው፡፡ ደሞዝ ከባንክ አካውንት ገባ፡፡ የባንክ የገንዘብ ማውጫዎች ሥራ እንደያዘ ልጅ፣ ከገንዘብ ማስገቢያዎች የበለጠ ተፈላጊነታቸው ጨመረ፡፡ ኪስ በገንዘብ ሞላ፡፡ የተወሰነ ዕዳም ተከፍሎ-የቀረዉ ለሚቀጥለው ወር ተዛወረ፡፡ ሆድም አዲስ ነገር አየ፡፡ በሰሞነ ህማማት የተገባዉ ቃል ማስፈጸሚያ ይሆን ዘንድ ባለፈዉ ወር ተገዝቶ ሣይሰራ የተቀመጠው አስቤዛ ላይ ጭማሪ አስቤዛ ተገዛ፡፡ እቤት አብስለን እንብላ የሚል ቢጠፋም፤ ወዳጅ ዘመድም በዛ፡፡ መለኪያ ተሞላ፡፡ ብሉልኝ ጠጡልኝ ተባለ፡፡ በስንት ልመናና እግዝዮታ አልታረቅም ብላ ያኮረፈች የሴት ጓደኛም ሆድዋ ተፈቶ፣ ቅያሜዋ ጠፍቶ እራሷ ደውላ መጣች፡፡ ሳምንትዋም የተቀደሰች-ቅድስት ሆነች!፡፡ መስቀልያ ሠርቶ በጊዜ አናት ላይ በቆመዉ ወር ላይ ያለው ተቀጣሪ ግን አሁንም ደጋግሞ ይጮሀል
‹‹አቤቱ የምሠራውን አላውቀውምና ይቅር በለኝ››፡፡  

ኒቆዲሞስ
ሦስተኛዉ ሳምንት፡፡ የሞላዉ ጎደለ፡፡ ከአፋፍ ቆሞ ‹‹ኪሱን ጉደል ብለዉ አለኝ በኒቆዲሞስ›› እያለ ዋሽንት ይጫወት የነበረው ችግርም በተሸረሸረው ላይ ተረማምዶ ከእነ ችግሩ ወደ ጓዳ ዘለቀ፡፡ ወዳጅ ዘመድም እራቀ፡፡ ቶሎ ቶሎ የሚከፋት የሴት ጓደኛም ያለውን ከፍለዉ እንደሸጧት ከመጨረሻው ወጪ ጋር ከቤት እንደወጣች ቀረች፡፡ በየወሩ እየተጨመረ ከጓዳ ዲብ የሠራውን አስቤዛ ወደ ምግብነት የመቀየር ጥረት ተጀመረ፡፡ አብስሎ ከመብላቱ ሽንኩርት እየላጡ ማልቀሱ ባሰ! እንባው የሽንኩርቱ ብቻ አይደለም፡፡ ከማጣት በላይ ምን የሚያስለቀስ አለ? (ሐዘን ላይ ማልቀስ-የሚወዱትን ማጣት፡፡ ታሞ ማልቀስ-ጤና ማጣት፡፡ ቤት ዘግቶ ማልቀስ-እሷን ወይ እሱን ማጣት፡፡ ሽንኩርት እየላጡ ማልቀስ-የበሰለ ነገር ወይ ምታበስል ማጣት።) ደግሞስ ሽንኩርት እያላጡ ካለቀሱ፤ ሲከትፉ ምን ሊሆን ነዉ? እሱም ብርቅ ሆነና ከሁለት ቀናት በኋላ ግን ማብሰያው ከየት ይምጣ? ኒቆዲሞስነት ብቻ ቀረ፡፡ ሲገድ ደመወዛቸውን እንደ ደምና ወዛቸው ከሚቆጥቡት ጋር ተመሳስሎ ሥቆ፤ እጥፍ እያሉ በለጋሾችና አበዳሪዎችን ዙርያ ጭራ መቁላት ተጀመረ፡፡  የባሰ አታምጣ አሉ!  መስቀልያ ሠርቶ በጊዜ አናት ላይ በቆመው ወር ላይ ያለው ተቀጣሪ ግን አሁንም ደጋግሞ ይጮሀል፡-
‹‹አቤቱ የምሠራዉን አላውቀውምና ይቅር በለኝ››፡፡   
ሆሳዕና
ለወሩ መዳረሻ የሚሆን ገንዘብ ከኪሱ የተረፈዉ እርሱ የተመሰገነ ነዉ፡፡ ሆሳዕና-የህማማት መባቻ፡፡ መጨረሻው፤ የማይታወቀው አምሳለ ሲኦል፡፡ ወደ ስቅለት መንደርደርያ፡፡ ካለፉት ሦስት ሳምንታት ቀናት ድምር የሚበልጡ እረጅምና የማያልቁ ቀናት፡፡ ከችጋር በቀር ሁሉም የሚርቅበትና ጀርባቸውን የሚሰጡበት፡፡ ቀናቶቹም ይከፋፈላሉ። የመጀመርያው ቀን አባካኝነት የተረገመበት ቀን፡፡ ሁለተኛው ቀን፣ የጥያቄ ቀን፡፡ ለምን?...እንዴት?...በምን ሀጥያቴ? የሚባልበት ምሬት የበዛበት ቀን። ቀጣዩ ቀን የምክር ቀን፡፡ እንዴት ላድርግ? ምን ይሻለኛል? የሚባልበት ቀን፡፡ ከሱ ቀጥሎ ያለው ቀን ጸሎተ ሐሙስ፡፡ ተሸናፊነት ታውጆ አጽናኝ፣ አበርታኝ የሚባልበት፤ እርዳታ የሚጠየቅበት። ተከታዩ ቀን ስቅለት የሚጀምርበት!፡፡ ስቅለት የሚጸናበት! አባት ሆይ፤ ለምን ተውከኝ የሚደገምበት፡፡ ክፋቱ ሰቃዮቹ ኪስን በጦር ቢወጉት ጠብ የሚል ነገር የለም! ከንፈር በችጋር እንዲያ ተሰነጣጥቆ እያዩ እንኳን ሀሞትና ከርቤ በሰፍነግ ሞልተው፣ በሁሶፕም አድርገው ወደ አፍ ለመስደድ ይስገበገባሉ፡፡ ብቻ የማዘጋጀት ቀንን አልፎ ዘወረደ እየመጣ ነዉ፡፡  መስቀልያ ሠርቶ በጊዜ አናት ላይ በቆመው ወር ላይ ያለው ተቀጣሪ ግን አሁንም ደጋግሞ ይጮሀል፡-
‹‹አቤቱ የሚሠሩትን አያውቁምና ይቅር በላቸው!››     

Saturday, 20 January 2018 12:07

የረጋ ወተት ቅቤ ይወጣዋል!

ከዕለታት አንድ ቀን፤ የዱር አራዊት ስለ እድራቸው ለመወያየት እንደተሰበሰቡ፤ የአንበሳ ድምፅ ከወደ ጫካው ይሰማል፡፡ ስብሰባቸውን አቋርጠው፤
“ኧረ ንጉሥ አንበሳ ይጮሃል፡፡ ምን ሆኖ ይሆን?” አለ አንደኛው፡፡
“ሲያገሣ ይሆናል ባንጨነቅ ይሻላል” አለ ሌላው፡፡
“ኧረ ግዴላችሁም፤ ጩኸቱን እየሰማችሁ ለምን ዝም አላችሁ፤ ብሎ ይጨርሰናል፡፡ ኧረ እንሂድና ምን ሆነሃል እንበለው” አለ ሶስተኛው፡፡
ጥቂት እንደተከራከሩ፣ ጦጢት፤
“አንሂድ፡፡ ለምን እንደጮኸ ሳናውቅ ምን አስኬደን?” አለች፡፡
“ምንም ይሁን ምን፤ ንጉሣችን ነው፡፡ ንጉሥን መፍራት ያስፈልጋል” አለ፤ አንድ ትጉ አውሬ፡፡ እንሂድና እንየው የሚለው ሀሳብ አሸናፊ ሆነና ሁሉም ወደ አያ አንበሶ ሄዱ፡፡
አያ አንበሶ ታሞ የመጨረሻው ሰዓት ላይ ደርሶ ኖሯል የሚጮኸው፡፡ አውሬዎቹ ሌላ ውይይት ጀመሩ፡-
“ማነው አያ አንበሶን ተክቶ የሚወርሰው?” አለ አንደኛው
“ነብር” አለ ሁለተኛው
“ነብር በጣም ይሞነጭራል”
“ዝሆን!”
“ዝሆን ቀርፋፋ ነው አይመራንም”
“ጎሽ”
“ጎሽ አይሆንም፡፡ ለልጁ ሲል ማንንም ይወጋል- በማንም ይወጋል”
“ታዲያ ማን ወራሽ መሪ ይሁን?”
ጦጢት ጣልቃ ገብታ፤
“እስቲ አያ አንበሶ መጀመሪያ በወጉ ይሙት? እስቲ ጥቂት ጊዜ እንጠብቅ”
“አንቺ ደግሞ ጊዜ ጊዜ ጊዜ ትያለሽ፡፡ ከሞተ በኋላ ከምንጨቃጨቅ አሁኑኑ ብናስብበት አይሻልም” አለ ነብሮ፡፡
“እኔ‘ኮ ከትላንት ወዲያ ነው ስለ ወንበሩ እንነጋገር ያልኩት፡፡ ያኔ እሺ ብላችሁኝ ቢሆን ይሄ ሁሉ መደናበር ባልኖረም ነበር- አሁንም የአያ አንበሳን የመጨረሻውን ቃል እንስማ!”
አያ አንበሶ እያቃሰተ የመጨረሻውን ኑዛዜውን ተነፈሰ፡-
“ዙፋኔን የሚወርሰው ልጄ ደቦል ነው!” አለ፡፡
“በቃ ተገላገልን፡፡ ወራሽ ገዢያችንን አወቅን!” አለ አንዱ፡፡
“አልጋ ወራሽ መኖሩ ታላቅ ዜና ነው”
ይሄኔ ጦጢት፤
“ደቦል የታለ?”
“አያ አንበሶ ልጅ ሳይኖረው ወራሼ አይልም፡፡ አንቺ ደግሞ ጭቅጭቅ ትወጃለሽ፡፡”
“ምናለበት ይምጣና እንየው፡፡ መሪያችን ከሆነ በሜዳ ስሙ ሳይሆን ይምጣና ራሱን ያስተዋውቀን!”
“ሰባት ዓመት አፅሙ የገዛን ንጉሥ በነበረበት ዓለም ደቦል ታየ አልታየ ምን ያነታርከና?”
“ዕውነቱን ነው! ዕውነቱን ነው! ዕውነቱን ነው!” ሁሉም ጮኹ፡፡
በማህል አያ አንበሶ፤
“አቅም እየተሰማኝ፣ ነፍስ እየዘራሁ ነኝ! እንኳን ደስ አላችሁ!”
ሁሉም በየሆዱ፤
“ይሄም አለ እንዴ?!”
ጦጢት ብቻ ሳቋን ለቀቀችው!
*    *    *
የጊዜ ግምት የሁልጊዜ ችግራችን ነው፡፡ አለማሰብ የሁልጊዜ ችግራችን ነው፡፡ የተንገዳገደውን ወደቀ ማለት የሁልጊዜ ችግራችን ነው፡፡ በስሜት መነዳት እጅግ የጠና ችግራችን ነው፡፡ በራስ መተማመን ትተን በሌሎች ድክመት፣ መሰነጣጠቅና ገባ - ወጣ ላይ ተንተርሰን ዕጣችንን መወሰን ኋላ አባዜው ብዙ ነው! ምክንያቱም ዕድሜ ልካችንን በሰው እጅ የመጎሳቀልን ዕድል ለሌሎች አሳልፈን ሰጥተናል! የሚገርመው ቀጣይ ገዢ ፍለጋ በየማዕዱ መጨቃጨቃችን ነው፡፡ ብዙ ጊዜ ብለነዋል፤ ሰሚ ከጠፋ ዛሬም እንደግመዋለን፡-
“… አሁን የት ይገኛል፣ ቢፈልጉ ዞሮ
መስማት ከማይፈልግ፣ የባሰ ደንቆሮ!”
አሁንም የህዝቡን የልብ - ትርታ እናዳምጥ!
“በጠበቧ ቢሮዋችን ተቀምጠን የሰፊውን ህዝብ የልብ ትርታ እናዳምጣለን” ያለው ደርግ፤ “ካላዳመጥከን ወዮልህ!” ወደ ሚል ቅኝት መለወጡን ከእነ ሙሉ ቃሉና ደሙ እናስታውሰዋለን!
“እንደሙሴ ታቦት፣ ዘውዱን ካናታችሁ
አሁንም ጭናችሁ፤
እናንተ ገዢዎች
እናንተ ደርጋሞች
ምነዋ አፌዛችሁ
ምነዋ ቀልዳችሁ!”
እስከማለት ተናግረን ነበር!
የኃይለ ሥላሴም መንግስት ቢሆን ከተረቶች ሁሉ የሚያደንቀው፤ “የዝሆን ጆሮ ይስጠኝ”ን ነበር! 3ኛ ክፍለ ጦር አመፀ - ምላሹ ዝም! የአርሲ፣ የባሌ፣ የጎጃም አርሶ አደር አመፀ - ጭጭ ማለት ወይም ጭጭ ማድረግ! ተማሪው ተነሳ - ተዉት የትም አይደርስም!
በመጨረሻ “ወሎ ተራበ፣ ተሰደደ‘ኮ” ሲባሉ “ወሎ መሰደድ ልማዱ ነው - ተዉት” አሉ አሉ፡፡
የወሎው ባለስልጣን ለገሠ በዙ!
ይሄ ሁሉ ማትጊያ ደወል (Death-bed) የንጉሡን መንግስት መንበሩን አልነቀነቀውም! የአንድ ቀን ቤንዚን ዋጋ መቀጠል (የዛሬውን አስባችሁ “እግዚኦ!” እንዳትሉ አደራ!) አየር እየበዛበት የተነፋፋውን የፖለቲካ ባሉን (ፊኛ) ጠቅ ሲያደርገው አብዮት ፈነዳ (Tipping point እንዲሉ) ያቺ ጠቅታ የብሶት፣ የምሬት፣ ክፉ ጥርቅም ውጤት ናት! በደርግ ጊዜ የዚሁ ብልልት ውጤት ነው የታየው! ዛሬም ያው ነው - ግን anachronistically (ጊዜና ቦታውን ያልጠበቀ ድምዳሜ) ሳናስበው፤ መከራን እንደማወዳደር ሳይሆን እንደጊዜው ባኮ (current package) እናስበው!
“ያለው መንግስት ይውደቅ” ስንል የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር እንዳሉት፤ ሟርት ባይሆንስ? የተቃዋሚ “አማራጭ አልባ” ትግል ባይሆንስ? የህዝብ መንፈስ ቢሆንስ? እና ቢሳካለ ማንን እንተካለን? መልሱን ከማንም አንጠብቅ - ከራሳችን እንጂ! ሮበርት ብራውን፤
“ደሞም ማወቅ ማለት …
ከውጪ ያለውን ሄዶ ከመፈለግ
ከውስጥ የበራውን እንዲወጣ ማድረግ!”
(ትርጉም ገ/ክርስቶስ ደስታ)
የሀገራችን ግራ መጋባት የሚጀምረው “የአብዬን እከክ ወደእምዬ ልክክ” ስንል ነው፡፡ ለማንም ላይጠቅም ሀገርና ህዝብን የመበደል ጥፋት ነው! ካለፈ በኋላ የሚቆጭ፤ ሳንማማር የመጨረሻችንን ጥርጊያ ጎዳና የሚያመቻች፣ ጥሬዎቹን የማያበስል፣ የበሰሉትን የሚያራግፍ የቤት ጣጣ! ሀገራችን ራዕይ የቅዠት ኑዛዜ የሆነባት የዕርግማን ቋት ናት! የሚበጇትን እየገፋች የሚንቋትን እያቀፈች፤ በራሷ ዛቢያ ላይ የምትሽከረከር ናት! ገና ረዥም መንገድ አለባት! የሚገርመው ሳይደራጁ እግርና እጅን አጣጥፎ መቀመጥ ለማን ይበጃል፡፡ ለመደራጀት የጋራ አመለካከት እንጂ አንድ ዓይነት መፍትሄ አይጠበቅብንም!   
ነገር ሁሉ እንደፈለግነው ቢሆን እንኳ እንዴት እንመራዋለን እንበል፡፡ የሌሎችን መውደቅ ስንመኝ፤ የእኛ መነሳትም ገና ዝግጅት እንደሚፈልግ፣ የአለመደራጀት ጣጣ መልሶ ለተደራጀ ወገን አሳልፎ እንደሚሰጠን አንርሳ! የ1966 ዓ.ም አብዮት ያንን ካላስተማረን፣ ያ ሁሉ የተከፈለው ደም ምንም ፍሬ አልነበረውም ማለት ነው፡፡ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ያሉትን አንዘንጋ፡-
“ያልተደራጀ ኃይል፤ ኃይል አይደለም!”
ለማንኛውም ቆም ብሎ ማሰብ፣ ረጋ ብሎ መወያየት፣ ካበደ ጋር አለማበድ ወደ መፍትሔ ያመራን ይሆናል፡፡ “የረጋ ወተት ቅቤ ይወጣዋል!”

  ከተመሰረተ 81 ዓመታት ያስቆጠረው አዋሽ ወይን አክሲዮን ማህበር፣ በቅርቡ ከሶማሌ ክልል ለተፈናቀሉ ዜጎች የ40 ቶን (400 ኩንታል) በቆሎና የ100 ሺህ ብር ድጋፍ ያደረገ ሲሆን ኩባንያው ማህበራዊ ኃላፊነቱን ለመወጣትም የተለያዩ ፕሮጀክቶችን ቀርፆ እየተንቀሳቀሰ መሆኑ ተገልጿል።
ኩባንያው ጥር 6 ቀን 2010 ዓ.ም 400 ኩንታል በቆሎና የ100 ሺህ ብር ድጋፍ በአርሲ ሮቤ ለሚገኙ ከ450 በላይ ተፈናቃዮች አስረክቧል፡፡
የድጋፍ ርክክቡ በተከናወነበት ወቅትም የአዋሽ አክሲዮን ማህበር የስራ አመራሮች ለህብረተሰቡ የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ያስታወቁ ሲሆን ሌሎች ኩባንያዎችም ይህን ልምድ በመቅሰም ለተፈናቃዮች በየፊናቸው ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ከሚላ፣ ጉደር፣ ገበታ፣ አዋሽ በተሰኙ የወይን ጠጅ ምርቶቹ የሚታወቀው አዋሽ ወይን አክሲዮን ማህበር፣ በአሁኑ ወቅት ሙሉ ለሙሉ በግል ባለሀብቶች ይዞታ ስር የሚገኝ ሲሆን በኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን መርቲ ወረዳ ላይ 517 ሄክታር መሬት ላይ ሰፊ የወይን እርሻ ባለቤትም ነው፡፡
በወይን እርሻው አካባቢ ለሚገኙ ከ200 በላይ አባወራዎች የተለያዩ ድጋፎችን በማድረግ ላይ እንደሚገኝ ያስታወቀው ድርጅቱ፤ በቅርቡ በዶሌ፣ ዶኬቻና መልኩ ቀበሌዎችን የንፁህ ውሃ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አስታውቋል፡፡ ቀደም ሲል ማህበረሰቡ የመጠጥ ውሃ ያገኝ የነበረው በቀጥታ ከአዋሽ ወንዝ ሲሆን ይህም ለውሃ ወለድ በሽታዎች ያጋልጥ እንደነበር ታውቋል። ድርጅቱ በ1.2 ሚሊዮን ብር የጋራ የንፁህ መጠጥ ውሃ መጠቀሚያ ቦኖ ለማህበረሰቡ ከማሰራቱም በተጨማሪ ለከብቶች የሚሆን የሰው ሰራሽ የኩሬ ውሃም አስቆፍሯል፡፡ በተጨማሪም የህፃናት ማቆያ ማዕከል መገንባቱንና የህክምና ክሊኒክ ግንባታዎችን  እያከናወነ መሆኑን ኩባንያው  አስታውቋል፡፡
በፀሐይ ኃይል የሚሰራ የኤሌክትሪክ አገልግሎትም ማህበረሰቡ እንዲያገኝና የአካባቢውን ወጣቶችም በተለያዩ የስራ መስኮች በድርጅቱ ውስጥ ቀጥሮ የስራ እድል ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ኩባንያው ጨምሮ ገልጧል፡፡  
አዋሽ ወይን አክሲዮን ማህበር በአሁኑ ወቅት በልደታና በመካኒሳ በሚገኙ ፋብሪካዎቹ በዓመት 10 ሚሊዮን ሊትር የተለያዩ የወይን ጠጅ መጠጦችን እያመረተ መሆኑ ታውቋል፡፡

 እናትነት …ሁሉም ነገር፡፡
እናት ካለች ቤተሰብ አለ፡፡ ቤተሰብ ሲኖር አካበቢ ወይንም መንደር ከዚያም አገር ይኖራል፡፡ አገር ካለ አለም እውን ይሆናል፡፡ እናት ደህና ካልሆነች ግን ሁሉም ነገር ይበላሻል፡፡
ዶ/ር ፈቃደ አየናቸው
በውጭው አቆጣጠር ከጃኑዋሪ 9/ እስከ ፌብረዋሪ 7/ በኢትዮጵያ አቆጣጠር ከጥር 1 እስከ ጥር 30 ድረስ ለአንድ ወር የሚቆይ የእናቶችን ደህንነት የሚመለከት Campaign ወይንም የተለያዩ ስራዎች የሚሰሩበት እቅድ ተነድፎአል፡፡
በርእስነት የተቀመጠው አባባል በእንግሊዝኛው <<…NO MOTHERHOOD…DURING CHILD HOOD…>> የሚለውን የዘንድሮው አገር አቀፍ የእናቶች ደህንነት የአንድ ወር ዘመቻ ካተኮ ረባቸው ነጥቦች አንዱ ነው፡፡ በዚህ አመት ሌላው በአጠቃላይ የእናቶች ደህንነትን በሚመለከት ለጉዳት ከሚዳርጉዋቸው ውስጥ የፊስቱላ ሕመም እንዲሁም የደም መፍሰስ እና በልጅነት በእርግዝና ምክንያት የሚከሰቱ ጉዳቶች ምን እንደሆኑ ጎልተው እንዲወጡ እና የሚመለከተው ሁሉ ትኩረት ሰጥቶ እንዲከላከላቸው የሚል እሳቤ የያዘ ነው። ይህንኑ መሰረት በማድረግም መልእክቶቹን ከተለያዩ ባለሙያዎችና የህክምና አገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ከሆኑት በማሰባሰብ ለአንባቢ እነሆ ብለናል፡፡
ዶ/ር ፈቃደ አየናቸው የማህጸንና ጽንስ ሕክምና እስፔሻሊስትና በሐምሊን ፊስቱላ ኢትዮጵያ የሆስፒታሉ ሜዲካል ዳይሬክተር ናቸው፡፡ እሳቸው እንዳሉት በእርግጥ በአገር ውስጥ ያሉ የፌስቱላ ታካሚዎች ምን ያህል ናቸው የሚለውን ለመለየት ወደሁዋላ በመመለስ የተደረጉ ጥናቶችን ማየት አስፈላጊ ቢሆንም የፌስቱላ ሕመም አሁንም ድረስ መኖሩን ግን ማረጋገጥ ይቻላል፡፡ በእርግጥ በተለያዩ ጊዜያት የተደረጉ ጥናቶች የሚያሳዩት ቁጥር ከፍ ዝቅ ቢልም ባሁኑ ወቅት ግን ከ5-7/ሺህ/ድረስ የሚሆኑ ኢትዮያውያን ሴቶች በዚህ ችግር ተጠቂ ናቸው የሚል ግምት አለ፡፡ ስለዚህም ፊስቱላ ሙሉ በሙሉ ጠፍቶአል የማይባል ሲሆን በአሁኑ ወቅት ግን በተለያዩ አካባቢዎች ማለትም ከህብረተሰቡ ጋር በቅርበት መስራት የሚያስችል አደረጃጀት ስላለ የተሸለ ነገር ይታያል፡፡ መንግስትም ፊስቱላን ለማጥፋት የሚል ፕሮግራም ነድፎ ሐም ሊን ፊስቱላ ኢትዮጵያም በግብረኃይሉ የሚሳተፍ ሲሆን የዚህ እቅድም በ5/አመት ጊዜ ውስጥ ፊስቱላ እንደዋነኛ የህብረተሰብ ጤና ችግር የማይሆንበት ደረጃ እንዲፈጠርና ለአዳዲስ ተጎጂ ዎችም አስፈላጊውን የህክምና እርዳታ በተገቢው መንገድ ማዳረስ ይገባል የሚል ነው፡፡
ዶ/ር ዋሲሁን አለማየሁ የማህጸንና ጽንስ ሕክምና እስፔሻሊስት እና በአሰላ Referral & teaching ሆስፒታል የፊስቱላ ሕክምና ክፍል አስተባባሪና ኃላፊ ናቸው፡፡ እሳቸው እንደሚሉት ፊስቱላ የሚከሰተው በዋናነት ከወሊድ ጋር በተያያዘ ሲሆን በተለይም በተራዘመ ምጥ ምክንያት ነው፡፡ አንዲት ሴት በምጥ ከ24/ሰአት በላይ ከቆየች በእራስዋም እንዲሁም በልጅዋ ላይ ችግር ሊፈጠር ይችላል፡፡  ከዚህም በተጨማሪ በቤታቸው በተራዘመ ምጥ ቆይተው ለእርዳታ ወደሆስፒታሉ የመጡ እናቶችን የማዋለድ ስራ በሚሰራበት ወቅት በተለያዩ መሳሪያዎች መጠቀምና ኦፕራሲዮን ማድረግ ስለሚኖር በዚያ ምክንያትም ለፊስቱላ የሚጋለጡ እናቶች እንደሚኖሩ እሙን ነው፡፡ ከዚህም ጋር ተያይዞ በሌሎች ምክንያቶች ማለትም ለምሳሌ ለካንሰር ሕክምና በሚደረጉ የቀዶ ሕክምና አገልግሎት ሳቢያ ፊስቱላ ሊከሰት ይችላል፡፡
በዚህ በእናቶች ደህንነት ምክንያት የሚነሳው ፊስቱላ ከማህጸንና ዙሪያውን ካሉ አካላት ጋር በተያያዘ አላስፈላጊ ቀዳዳ ሲፈጠር የሚታየውን ሲሆን ቃሉ ግን በማንኛውም የሰውነት ክፍል አላስፈላጊ ቀዳዳ ተፈጥሮ ሲታይ የምንጠቀምበት ነው፡፡ በእናቶች ላይ ስንመለከተው በማህጸንና በሽንት መሽኛ አካባቢ ወይንም በማህጸንና በሰገራ መውጫ አካባቢ የሚፈጠር ቀዳዳ ፊስቱላ ይባላል። ይህም በኢትዮጵያ ፊስቱላ የሚባለውን የጤና ችግር ከ90/በመቶ በላይ ድርሻ ይይዛል፡፡ በወሊድ ሰአት ልጁ በሚያልፍበት መንገድ ላይ እና በሽንት ፊኛው መሐል ላይ ለረጅም ሰአት ሲቆይ የደም ዝውውር ይዛባል፡፡ የደም ዝውውር ሲዛባ የሽንት ፊኛውና የወሊድ አካል ለረጅም ጊዜ ደም ስለሚያጣ ይጎዳል፡፡ ያ ክፍል ደም በማጣቱ ምክንያትም ስለሚሞት ይረግፋል፡፡ በሚረግፍበት ጊዜ በፊት ያልነበረ ክፍተት በሁለቱ መካከል ይፈጠራል። ያ ክፍተት ደግሞ ሽንት በማንኛውም ጊዜ ሴትየዋ ልትቆጣጠር በማትችልበት መንገድ ይፈሳል፡፡
ፊስቱላ መከላከል የምንችለው ነገር ነው፡፡ መከላል የሚቻል ነገር በመሆኑም ሁሉም ባለሙያውም ሆነ ህብረተሰቡ በቀበሌ ደረጃ ካሉት ጀምሮ የሚችለውን ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡ ከዚህ ባለፈ ሐኪሞቹ ችግሩ የገጠማቸው ሴቶች ሲመጡ ሕክምናውን ከመስጠት ባሻገር ያቺ የታከመች ሴት ከእራስዋ አልፋ ሌላዋን እናት ማስተማር እንድትችል አቅም ፈጥሮ ወደቤተሰብዋ መቀላቀል ተገቢ ነው፡፡ እየሰራን ያለነውም በዚህ መንገድ ነው፡፡
ጤና መኮንን ብርቄ ግርማ
ጤና መኮንን ብርቄ ግርማ እንደገለጹት በአሰላ ሆስፒታል የፌስቱላ ታካሚዎች የሚረዱት በአንድ ክፍል ውስጥ የነበረ ሲሆን ከማህጸንና ጽንስ ሕክምና ክፍል ጋር በተያያዘ ሕክምናው ይሰጥ ነበር፡፡ አሁን ግን ይህ ክፍል እራሱን ችሎ ባለሙያዎችም ለብቻ ተቀጥረው በማገልገል ላይ እንገኛለን፡፡ የፌስቱላ ሕክምና ክፍሉ የራሱ የሆነ 15/አስራ አምስት አልጋ ያለው ሲሆን በወር ውስጥ በአማካይ ከ6-10/ታካሚዎችን ያስተናግዳል፡፡ የታካሚዎች ሁኔታ እንደማንኛውም ታካሚ ከወቅት ጋር የሚያያዝ ሲሆን በክረምት እና በበጋው ወቅት ከፍና ዝቅ የሚልበት ሁኔታ ይስተዋላል፡፡ በተለይም በክረምት ወቅት እነዚህ ታማሚዎች ያሉበትን አካባቢ አቋርጠው ወደጤና ተቋሙ ለመምጣት ስለሚቸገሩ ባሉበት የሚቆዩ ሲሆን የቅስቀሳ ወይንም ትምህርት የመስጠቱን ነገር ተከትሎም ታካሚዎች ቁጥራቸው ከፍና ዝቅ የሚልበት ሁኔታ ይስተዋላል፡፡ ከጤና ጣቢያዎች ጋር በመሆን ከአሰላ ሆስፒታል የፊስቱላ ሕክምና ክፍልም እየሄድን አብረን ትምህርት እንሰጣለን፡፡ ፊስቱላ የተባለው የጤና ችግር የሚገጥማቸው በተራዘመ ምጥ ምክንያት ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ የመንገድ እርቀት፣ የገንዘብ እጥረት ወይንም ቀደም ሲል ከነበሩ ቤተሰቦች የህይወት ልምድ በመነሳት እቤት መውለድ ትክክለኛው ነገር ነው ብሎ በማሰብ በፍጥነት ወደ ጤና ተቋም አለመሄድ ለችግሩ መንስኤ ይሆናል፡፡ አንዳንዴ እቤት ውስጥ በተራዘመው ምጥ ቆይታ በአቅራቢያ ወደሚገኘው ጤና ጣቢያ ብትሄድም በማዋለድ ሂደቱ ላይ ፊስቱላ የሚከሰትበት አጋጣሚ ይስተዋላል፡፡ በተለይ ደግሞ ፊስቱላ የሚከሰተው በአብዛኛው በመጀመሪያ ልጅ መውለድ ጊዜ ሲሆን እነዚህ ለመጀመሪያ ጊዜ እርጉዝ የሚሆኑት በአብዛኛው በልጅነት እድሜያቸው የተዳሩና ያረገዙ ሴት ልጆች ናቸው፡፡ ፊስቱላ ብዙ ምክንያ ቶች ቢኖሩትም ቀደም ሲል የጠቀስናቸው በግልጽ የሚታዩ ናቸው፡፡
‹‹…እኔ የመጣሁት ከወላይታ ነው፡፡ ዛሬ 22/አመቴ ነው። ትዳር ከያዝኩ ወደ 7/አመት ይሆነኛል፡፡ ትዳር በያዝኩ ወቅት ወዲያው በአመት ጊዜ ውስጥ ነው ያረገዝኩት፡፡ ምጥ የመጣ ጊዜ ግን በጣም ተቸገርኩ፡፡ ወደጤና ጣቢያ እንዳይወስዱኝ ሩቅ ስለሆነ ይበል ጡኑ ትጎዳለች ብለው እቤት አስቀመጡኝ፡፡ ነገር ግን በአምስተኛው ቀን ትሞታለች ብለው በቃሬዛ ተሸክመው ወሰዱኝ፡፡ ጤና ጣብያ ስደርስ ልጄ ሞቶ ነበር፡፡ እኔም ሳልሞት ለጥቂት ነው የተረፍኩት። ከዚያም ወደቤቴ መለሱኝ፡፡ ሌላ ችግር ደግሞ ተከሰተ። ሽንቴን መቆጣጠር አልቻልኩም፡፡ ከሶስት አመት በላይ ሽንቴ ሲፈስ ይህ የእግዜር ቁጣ ነው ብለው ዝም ብለውኝ ነበር፡፡ በሁዋላ ግን ትምህርት የሚያስተምሩ ሐኪሞች ሲመጡ ጉዋደኛዬ የሆነች የጎረቤት ልጅ ጠቁማ ካለሁበት ድረስ መጥተው አዩኝ፡፡ ከዚያም በቀጥታ ወደሐምሊን ፊስቱል ሐኪም ቤት እንድመጣ ተደረገ፡፡ አሁን ሕክምና ተደርጎልኝ ድኛለሁ፡፡ በጊዜው ግን እንዴት አድርጌ እራሴን እንደማጠፋ ነበር የማስበው፡፡ እግዚአብሔር ይመስገን …ስንት አመት ከተሰቃየሁ በሁዋላ አሁን ድኛለሁ፡፡››
በሐምሊን ፊስቱላ ኢትዮፕያ ታካሚ  
አንዲት ሴት ቅድመ እርግዝና ምርመራ አድርጋ …በእርግዝናዋ ጊዜ ክትትል ሳታቋርጥ ወደሕክምና ተቋም ሄዳ በሰለጠነ ባለሙያ የምትወልድ ከሆነ …ፊስቱላ አይከሰትም። በየትኛውም አቅጣጫ የእናቶችን ጤና ለማሻሻል የሚሰሩ ስራዎች በሙሉ በተጉዋዳኝ የፊስቱላ መኖርንም እየቀነሱት ይመጣሉ፡፡
ዶ/ር ፈቃደ አየናቸው