Administrator

Administrator

በኢትዮጵያ በ1920ዎቹ የነበረው ታሪክ ዛሬ ሲያስቡት ተረት ይመስላል፡፡ የኢትዮጵያ የጦር-ባላባቶች፤ ሰው ኃይለሥላሴ የሚባል (ራስ ተፈሪም የሚባል ስም አለው) አንድ ወጣት በአሰርታት ዓመታት ውስጥ መሪ ሊሆን ማኮብኮቡን ሰሙ፡፡ ይሄ ጭምት መሳይ ዝምተኛ ሰው አገሪቱን የመቆጣጠር አቅም እንደሚኖረው ሊገባቸው አልቻለም፡፡ ሆኖም በ1927 ዓ.ም ኃ/ሥላሴ እያንዳንዱ በየተራ እንዲመጣና ታማኝነታቸውን በመግለፅ መሪያቸው መሆኑን እንዲያረጋግጡ አዘዘ፡፡
አንዳንዶች በጥድፊያ፣ አንዳንዶች ፈራ-ተባ እያሉ ትእዛዝ ሲፈፅሙ፤ የሲዳሞው ደጃዝማች ባልቻ ግን አሻፈረኝ አለ፡፡ ኃይለሥላሴ በተለመደው የጨዋና ግትር ዘዴው፤ ባልቻ እንዲመጣ ተማፀነው፡፡ ባልቻም “እታዘዛለሁ ግን በፈለኩት ጊዜ ነው የምመጣው፡፡ በተጨማሪም 10,000 ጦር ይዤ ነው ከአዲስ አበባ ወጣ ብዬ እምጠብቀው” አለ፡፡
ኃ/ሥላሴም፤ “ስለክብርህ የፌሽታ ግብዣ ላደርግልህ አስቤአለሁና፤ ተጋበዝልኝ” አለ፡፡ ባልቻ ግን ታሪክን ጠንቅቆ ያውቃልና የቀደሙት የኢትዮጵያ ነገሥታትና መሳፍንት ግብዣን እንደወጥመድ ሲጠቀሙበት እንደኖሩ ተገንዝቧል፡፡ ነቄ ነው፡፡ መታሰርም ሆነ መገደል የሚከተለው ከግብዣ በኋላ ነው፡፡
ደጃዝማች ባልቻ የግብዣውን ዓላማ እንደተረዳ ለመጠቆም “የምመጣው 600 ክብር ዘበኞቼን ይዤ ነው” አለ፡፡ ኃ/ሥላሴ ግን “እንዲህ ያሉትን ጀግኖችህንማ ማስተናገድ ለእኔ ክብር ነው” ሲል መለሰ፡፡
ባልቻ ክቡር ዘቦቹን ግብዣው ላይ እንዳይሰክሩና በተጠንቀቅ እንዲጠብቁ አዘዘ፡፡ ግብዣው ቦታ ሲደርሱ ኃ/ሥላሴ ታይቶ የማይታወቅ አቀባበል አደገ፡፡ ባልቻ “ማምሻውን ወደ ጦር ሰፈሩ መመለስ አለብኝ፤ አለበለዚያ ጦሬ አዲስ አበባን እንዲወርር አዝዣለሁ” አለ፡፡ ኃ/ሥላሴ ባለመታመኑ እንዳዘነ በመግለፅ፤ ይልቁንም ከግብሩ በኋላ የሚዘፈነው ዘፈን የሲዳሞን ጦረኛነት የሚያረጋግጥ እንዲሆን አደረገ፡፡ ባልቻም ኃ/ሥላሴ የፈራና ለማይረታው ወታደሩ እጁን የሰጠው መሰለው፡፡
ከሰዓት በኋላው ሲገባደድ ባልቻና ወታደሮቹ ነጋሪት እያስጐሰሙ ወደ ጦር ሠፈራቸው አመሩ፡፡ ከሳምንታት በኋላ አዲስ አበባን መውረር እንደሚችል አሰበና ባልቻ ኃ/ሥላሴ እንግዲህ ቦታው ወይ ዘብጥያ ወይ ሞት ነው” አለ፡፡
ሆኖም ባልቻ ወደ ጦር ሠፈሩ አካባቢ ሲደርስ አንድ የተሳሳተ ነገር መኖሩን ተገነዘበ፡፡ አንድም ድንኳን የለም፡፡ የሚታየው ጭስ ብቻ ነው፡፡ አንድ የዐይን ምስክር የሆነውን ሁሉ አስረዳው፡- የኃ/ሥላሴ ጦር ባሳቻ መንገድ መጣ፡፡
የመጣው ግን ሊዋጋ አልነበረም፡፡ ኃ/ሥላሴ በዘምቢል ወርቅና ብር አጭቆ የላከው ጦር ነው፡፡ የባልቻን ወታደሮች መሣሪያ ሁሉ በወርቅና በብር ገዛ፡፡ እምቢ ያሉ ተያዙ፡፡ በጥቂት ሰዓት ውስጥ የባልቻ ጦር መሣሪያውን አስረከበ፡፡ ባልቻ ወደ ደቡብ 600 ወታደር ይዞ ለመሸሽ ቢፈልግም ያ መሣሪያ የወሰደባቸው የኃ/ሥላሴ ወታደር መንገዱን ገትሮ ይዟል፡፡
ወደ አዲስ አበባ እንዳያቀና ሌላ ጦር መንገዱን ገድቦታል፡፡ እንደቼዝ ተጨዋች ዙሪያውን ተከበበ፡፡ ባልቻ ለመጀመሪያ ጊዜ እጁን ሰጠ፡፡ በኩራትና በአጉል ምኞት የሠራው ኃጢያት ስለፀፀተው ወደ ገዳም ሊገባ ተስማማ፡፡ ያለ አንዳች የጥይት ድምፅ ኃ/ሥላሴ ደጃዝማች ባልቻን አስወገደ፡፡
የሲዳሞው ደጃ/ባልቻም ወደ ገዳሙ ከመግባቱ በፊት፤
“የተፈሪን ጉልበት አትናቁ፡፡ እንደ አይጥ ይድሃል፡፡ ሆኖም የአንበሳ ጥርስ ነው ያለው!” አለ፡፡
***
በግብዣ ከመጠመድ ይሰውረን! የሌሎችን ጉልበት ከመናቅ አባዜ ያድነን፡፡ የራስን አቅም የዓለም መጨረሻ ነው ብሎ ከማጋነን ይሰውረን! የመስተዋት መስኮቱን ጭሳማ የማድረግ ጥበብ ያለው አለቃ ወይም የፖለቲካ መሪ፤ ጭሳማውን ቀለም የበለጠ ባጠቆረው መጠን፣ የበለጠ እንዳናየው እያደረገ መሆኑን አንርሳ፡፡ “ጦርነቱን ከማወጅህ በፊት ድልን ተቀዳጅ” ይላሉ ፈረንጆች፡፡ እቅድህን አታሳውቅ፡፡ ስለእቅድህ ከመፎከር ተጠንቀቅ ነው ነገሩ፡፡ ባላንጣህ እቅድህን እንዳያውቅ ባደረግህ ቁጥር የድልህ መጠን ይበልጥ እየሰፋ ይመጣል፡፡ ስለእቅድህ በፎከርክ ቁጥር ግን ስኬትህን እያራቅህ ነው የምትሄደው፡፡ የሞቀ ከተማ እያሰብን መጨረሻችን ገዳም የሚሆነው ሥር-ባልሰደደ ድል ስንኩራራና ሌሎች ስለእኔ ምን ያስባሉ ብለን ሳንጠይቅ ስንቀር ነው፡፡
በቡድናዊ ስሜት አለመጠመድና አለመጨፈን ለአገርና ለህዝብ የሚበጅ አካሄድ ነው፡፡ ምክንያቱም አስተሳሰባችንን እያጠበብን የቡድናዊ ስሜት ተገዢ ስንሆን ደባንና ሴራን የሙጥኝ ወደማለት እንገባለን፡፡ ያ ደግሞ አደገኛ ነው፡፡
የሦስተኛው ክፍለ - ዘመን ህንዳዊ ፈላስፋ - ካውቲላ፤
“በዓላሚ ቀስተኛ፣ የተሰደደ ቀስት
አለው አጋጣሚ፣ ወይ ሊገል ወይ ሊስት፡፡
ግን በስል-ጭንቅላት፣ ሤራ ከተሳለ
ህፃንም ይገድላል፣ እናት ሆድ ውስጥ ያለ፡፡”
የሚለን ለዚህ ነው፡፡
ሌላው የአገር ጉዳይ ግልብ - እውቀትን መከላከል ነው - ባልበሰለ አዕምሮ ዘራፍ ማለትን፡፡ ያለፖለቲካዊ ብስለት ፖለቲከኛ ነኝ ማለትን፡፡ መላው ዓለም እውቀት ሆኖ ሳለ የአዕምሮን በር ዘግቶ፣ የእኔ እውቀት ብቻ ነው ገዢ ብሎ ማሰብ ክፉ አባዜ ነው፡፡ ከሳጥኑ ውጪ (Out of the box እንዲሉ) ለማየትና ለማስተዋል አለመቻል፤ የሌሎችን ሀሳብ ለመቀበል ዝግጁ አለመሆንን ያስከትላል፡፡ ያ ደግሞ ብዙ አለመግባባቶችን ይወልዳል፡፡ “ከመርገምት ሁሉ የከፋው መርገምት ቋንቋ ለቋንቋ መጠፋፋት” ይለዋል ባለቅኔው፡፡ ወጣቱ፤ መሰረታዊ እውቀት፣ ጥልቀትና ብስለት፣ ከዚያም ስክነትና ጥበበኛነት እንዲኖረው ለማድረግ ብርቱ ጥረት ያስፈልጋል፡፡ አዋቂው ራሱን እንዳያጥርና እንዳይገድብ፣ ልምዱን እንዲያጋራ መንገድ መክፈት ያሻል፡፡
ለሁሉ የህይወት ዘርፍ ፖለቲካዊ ትርጉምና አንድምታ ሰጥተን አንችለውም፡፡ መሰረታዊ እውቀት፣ ከኑሮ የምንቀስመው ልምድና ከባህል ያበለፀግነው የአእምሮ ሀብት የህይወትን ትርጉም ለማየት በዋናነት መሣሪያዎቻችን ናቸው፡፡ ይህንንም ለመቀበል እውነተኛ የህዝብ ፍቅር ያስፈልጋል፡፡ እውነተኛ የህዝብ ፍቅር የራስን ጥቅም መሰዋትን ይጠይቃል፡፡
“ህዝብን በመጠቀም የራስን ግብ ለመምታት ያለው ዘዴ በጉልበትና በማጭበርበር የሚደረግ ነው፡፡ ይልቁንም የህዝብ ፍቅር አንዱ መሣሪያ ነው ይላሉ ጠበብት፡፡ ያ ግን ፀሀይ እስኪወጣ መጠበቅን ይጠይቃል፡፡ ህይወት ደግሞ እያንዳንዷን ቅፅበት ትፈልጋለች” ይላል ጐይቴ፡፡
ካለፉት የወረስነው፣ ወይም የወረስን የመሰለንን ነገር ልብ ብለን እንመርምር፡፡ ለህዝብ ሰጥተነዋል ያልነውን ነፃነት፣ የኢኮኖሚ ብልፅግና፣ ፍትሕ-ርእዕ፣ ዲሞክራሲና እኩልነት እንመርምር፡፡ ስትራቴጂ በነደፍን፣ መመሪያ ባወጣን፣ ሪፖርት ባቀረብን ቁጥር ምን ያህል ለህዝብ ጠቀመ? ከሚለው ማንፀሪያ አኳያ እናስተውለው፡፡ መለስ ብለን፤ ያለምነውን ነገር፣ እጅ-ካስገባነው ነገር እናወዳድር፡፡ አለበለዚያ፤ የማታ ማታ “የዝንጀሮ ልጅ ቅቤ ተቀብተህ ና ቢሉት፤ ቅቤ ቢኖር ያባቴ ታፋ ይህን ይመስል ነበር ወይ” አለ እንደሚባለው እንዳይሆን እናስብ፡፡

ለፓትትሪያርክነት ይታጫሉ ተብለው የተጠበቁ ሊቃነጳጳሳት አልተካተቱም
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ÷ በፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴው ተለይተውና ተጣርተው በሚቀርቡለት አምስት ዕጩ ፓትርያሪኮች ላይ ዛሬ መወያየት ይጀምራል፡፡
ለምልአተ ጉባኤው ስብሰባ በሀገር ውስጥና በውጭ የተመደቡ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የሚገኙ ሲኾን አስመራጭ ኮሚቴው ባወጣው የምርጫ መሪ ዕቅድ መሠረት፣ ለዕጩ ፓትርያሪክነት ይኹንታ ያገኙ አምስት ዕጩ ፓትርያሪኮች የካቲት 18 ቀን 2005 ዓ.ም ለሕዝቡ ይፋ የሚደረጉበት ውሳኔ የሚተላለፍበት ይኾናል፡፡
የፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴው ከቤተ ክርስቲያኒቱ ካህናትና ምእመናን የተገኙትን ጥቆማዎች እንደ ግብአት በመያዝና በፓትርያሪክ ምርጫ ሕጉ የሰፈረውን ድንጋጌ በመጠቀም እንደለያቸው የተነገሩትን ዕጩ ፓትርያሪኮች ዝርዝር ለቅ/ሲኖዶሱ የሚያስረክበው በዛሬው ዕለት እንደኾነም ታውቋል፡፡ ኮሚቴው የዕጩዎቹን ዝርዝር ለቅ/ሲኖዶሱ ከማቅረቡ ቀደም ብሎ የወጡ መረጃዎች በዕጩ ፓትርያሪክነት የተመረጡት አምስት ሊቃነ ጳጳሳት÷ በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማትያስ፣ የወላይታ ዳውሮ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፣ የባሌ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የከፋ ሸካ ቤንች ማጂ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል እንዲሁም የሰሜን ጎንደር ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ናቸው፡፡
በዕጩዎች ዝርዝር ውስጥ ለፓትርያርክነት ይበቃሉ ተብለው ከታሰቡት ሊቃነ ጳጳሳት÷ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል፣ ብፁዕ አቡነ ገብርኤል፣ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ እና ብፁዕ አቡነ ጎርጎሬዎስ መካከል የተወሰኑት አለመካተታቸው የምርጫውን ሂደት የሚከታተሉ አካላትን አነጋግሯል፡፡ አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች፣ የሚጠበቁት አባቶች በዝርዝሩ ላለመካተታቸው በምርጫው ዙሪያ ያሳስበናል የሚሉትን የቡድን እንቅስቃሴዎች በምክንያትነት ይጠቅሳሉ።

በዲያቆን ዳንኤል ክብረት በተደረሰው ”ጠጠሮቹ እና ሌሎችም ወጐች” የተሰኘ መፅሃፍ ላይ ነገ ከቀኑ 8 ሰዓት እስከ 11 ሰዓት በብሔራዊ ቤተመዘክር አዳራሽ ውይይት እንደሚካሄድ ሚዩዚክ ሜይዴይ አስታወቀ፡፡ ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ በማቅረብ የሚመሩት ሃያሲና ወግ ፀሐፊ መስፍን ሃብተማርያም ናቸው፡፡

 

ከትላንት በስቲያ በመላው ዓለም የተከበረውን የቫለንታይን (የፍቅረኞች ቀን) አስመልክቶ ነገ ከጧቱ ሦስት ሰዓት እስከ ቀኑ 10 ሰዓት በጃንሜዳ ፍቅረኛን በጀርባ አዝሎ ውድድር እንደሚያካሂድ “ኪዩፒድ” የማስታወቂያ ሥራ አስታወቀ፡፡ ውድድሩ ከ18 አመት በላይ የሆኑ ጥንዶች ብቻ እንደሚሳተፉ ታውቋል፡፡ ኪዩፒድ ከአዲስ አበባ አስተዳደር ስፖርት ኮሚሽን ጋር በመተባበር ባዘጋጀው ውድድር ላይ አስር ሺህ ጥንዶች ይገኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ድርጅቱ ገልጿል፡፡ “ልዩነታችን መወሰናችን” በሚል መሪ ቃል በሚካሄደው ውድድር ላይ ነፃ የኤችአይቪ ምርመራና የምክር አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን ፕሮግራሙ ሩጫ፣ እግር ኳስ፣ ጠረጴዛ ቴኒስና የኢትዮጵያ ባህላዊ ጨዋታዎች እንዲሁም የዘፈን ግብዣ እንደሚያካትት አዘጋጆቹ ጠቁመዋል፡፡

Saturday, 16 February 2013 13:50

“Eyes and Mist” ዛሬ ይመረቃል

ተስፋ በተጣለበት ፓን አፍሪካዊ ፀሐፊ ታሪኩ አባስ እቴነሽ የተፃፈው “Eyes and Mist” ኤክስፐርመንታል ረዥም ልቦለድ ዛሬ ምሽት በጁፒተር ኢንተርናሽናል ሆቴል እንደሚመረቅ አፍሪቅያህ ሚዲያና ኮሙኒኬሽን አስታወቀ፡፡ ልብወለዱ ጭብጡን በወቅቱ ተጨባጭ እውነታ ላይ በማድረግ በእንግሊዝኛ የተፃፈ እንደሆነ ታውቋል፡፡ በምረቃው ላይ በአዲስ አበባ የሚገኙ የውጭ ሀገር ዜጐች፣ ደራሲዎችና ሌሎች ታዋቂ ሰዎች እንደሚገኙ የሚጠበቅ ሲሆን መፅሐፉ በባህር ዳር እንዲሁም በሰርቢያ፣ አሜሪካና ቱርክ እንደሚመረቅም ለማወቅ ተችሏል፡፡

በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተውና በሊዛ ተሾመ የተደረሰው “ፍትህን በራሴ” ረዥም ልቦለድ መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ 248 ገፅ ያለው መፅሐፍ በሀገር ወስጥ 40.50 ብር፣ በውጭ ሀገራት ደግሞ 10 ዶላር እየተሸጠ ሲሆን ደሪሲዋ መታሰቢያቱን ለወሲብ ጥቃት ተጎጂዎች  አድርጋለች፡፡ መፅሐፉ በኢንተርናሽናል ሊደርሺፕ ኢንስቲትዩት ማተሚያ ቤት የታተመ ሲሆን  ደራሲዋ ካሁን ቀደም “አሜከላ ያደማው ፍቅር” የተሰኘ መፅሐፍ ለንባብ አብቅታለች፡፡

አሁን በህይወት በሌሉት ታዋቂው ገጣሚ ዮሐንስ አድማሱ የተዘጋጀው “የቀኝ ጌታ ዮፍታሔ ንጉሤ አጭር የሕይወቱና የጽሑፉ ታሪክ” የተሰኘ መጽሐፍ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመጻሕፍት ዝግጅት ተቋም የፊታችን ረቡዕ በ10፡30 በብሔራዊ ቴአትር እንደሚመረቅ ተገለፀ፡፡ መጽሐፉን የገጣሚ ዮሐንስ አድማሱ ወንድም የሆኑትና ባለፈው ሳምንት ሕይወታቸው ያለፈው ዶ/ር ዮናስ አድማሱ ኤዲት እንዳደረጉት ታውቋል፡፡ በመጽሐፉ ምረቃ ዕለት ከዮፍታሔ ንጉሤ ሥራዎች ተቀንጭበው የሚቀርቡ ሲሆን፤ ዮፍታሔ የደረሰውን “አፋጀሽኝ” ትያትርን ለመጀመሪያ ጊዜ የተወኑት አቶ በለጠ ገብሬ ይገኛሉ፡፡ ከአቶ በለጠ ሌላ አርቲስት ሃይማኖት አለሙ በመርሃ ግብር አስተዋዋቂነት፣ ደራሲና ሃያሲ አቶ አስፋው ዳምጤ እና ፕሮፌሰር ሺፈራው በቀለ ስለ መጽሐፉ አስተያየት፣ ፕሮፌሰር ማስረሻ ፈጠነ ስለ ሕትመቱ እንዲሁም ዶ/ር ያዕቆብ አርሳኖ ንግግር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

* ተቃዋሚዎች የመሰብሰቢያ አዳራሽ የሚያከራየን አጣን አሉ!
* የሆቴል ባለቤቶች “ለምን እንደጭራቅ ፈሩን” ብለው ራሳቸውን ይጠይቁ!

በተለያዩ ጊዜያት ከአገራችን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር የመገናኘትና ኢንተርቪው የማድረግ ውጤት አልባ ሙከራዬን በተመለከተ በማቀርባቸው መጣጥፎች የተነሳ አንድም ትላልቅ ባለስልጣናትን የማግኘት ከፍተኛ ረሃብ አሊያም ወደ ፖለቲካው ሙያ የመግባት ፅኑ ፍላጎት እንዳለኝ የሚያስቡ የዋሆች አይጠፉም ብዬ እገምታለሁ፡፡ (ሥራዬን በአቋራጭ ማመልከቻ እንደማስገባት እየቆጠሩት) እነሱ ይሄን ማሰባቸው ኃጢያት ነው የሚል አቋም ባይኖረኝም በመርህ ደረጃ ሃሳባቸው የአመለካከት ችግር ያለበት መሆኑን በማያዳግም መልኩ መንገር ተገቢ ነው ብዬ አምናለሁ (የኢህአዴግን መግለጫ መሰለ አይደል?) እናላችሁ --- ለእኒህ የዋሆች አንድ ቀልድ አዘል ቁምነገር ልነግራቸው ፈለግሁ (እንደኢህአዴግ መፈረጅ ስለማልወድ ነው!)
ከጥቂት ዓመታት በፊት የሆነ ነው፡፡ አንድ ወጣት ሚኒባስ ታክሲ ውስጥ ኀይሌ ገብረሥላሴ ወደ ፖለቲካው ሊያተኩር ነው የሚለውን ወሬ ጮክ ብሎ ለጓደኞቹ ያወራል፡፡ ከጓደኞቹ መካከል ይህንን ጨዋታ ከጎኑ ለተቀመጡ አዛውንት ሊያጋራ የፈለገው ወጣት ወደሳቸው ዞር ብሎ -
“ይህን ታሪክ ሰሙ አባባ?”
“የትኛውን?”
“ኃይሌ ገ/ሥላሴ “ሩጫውን ትቼ ፖለቲካው ላይ ላተኩር ነው የምፈልገው” አለ የተባለውን”
“ምን ነካው እሱ ደሞ ---- ከእውነት ወደ ውሸት ይሄዳል እንዴ?” ሲሉ ዘበቱ አዛውንቱ፡፡
መቼም የአገር ሽማግሌ አይጥፋ ነው (እንደ ኀይሌ የሚሰማ ሲገኝ ነዋ!) ይሄው ከዚያ ወዲህ ጀግናው አትሌታችን “ፖለቲካ ለምኔ!” በማለት ሙያው ላይ አተኩሮ በመትጋት ላይ ነው - እውነቱ ላይ ማለት ነው፡፡ ለነገሩማ የፖለቲካ ጠበኞች አስታራቂ ሽማግሌ ሆኖም አይቶታል - ፖለቲካ ውሸት (የዋሾዎች) መሆኑን፡፡
የ97 ምርጫን ፖለቲካዊ ቀውስ ተከትሎ፣ ከየቤታቸውና ቢሮአቸው ተለቃቅመው የታሰሩትን (ኢህአዴግ “ራሴን ከናዳ ለማዳን ነው ያሰርኳቸው” ብሏል!) የቅንጅት አመራሮች ለማስፈታት የተቋቋመው የአገር ሽማግሌዎች ኮሚቴ አባል እንደነበረም አይዘነጋም፡፡

(አንዳንድ በ97 ምርጫ የተዘረሩ የኢህአዴግ አባላት “ቅንጅት” የሚለውን ቃል ሲሰሙ ይበረግጋሉ የሚባለው እውነት ነው እንዴ?)
አትሌት ኃይሌ በሽምግልና ሰበብ ወደ ፖለቲከኞቹ መቅረቡ ትልቅ ተመክሮ ሳይሰጠው የቀረ አይመስለኝም - የሦስተኛ ዓለም ፖለቲካን እርም ለማለት!! (ሩጫ ነፃነት ይፈልጋል አቦ!) ይሄን ሁሉ ያመጣሁት መቼም ለምን እንደሆነ ሳትገነዘቡ አትቀሩም ብዬ አምናለሁ፡፡ እኔም ከኃይሌ ተምሬአለሁና ፖለቲከኛ ወይም ባለሥልጣን የመሆን ህልምና ምኞት የለኝም ልላችሁ ፈልጌ ነው (ፖለቲካ ኪሳራ እንጂ ትርፍ የለውም ያለው ማን ነበር?) ግን ደግሞ የአገሬ ጉዳይ ያገባኛልና ኪሳራ ቢሆንም ፖለቲካ ማውራቴ፣ ፖለቲከኛ ማማቴ (ሱስ እኮ አይደለም!) አይቀርም - ምርጫ ስለሌለኝ (ፖለቲካ እንጀራዬ ነዋ!)
“የአገሬ ጉዳይ ያገባኛል” የምትለዋ ሐረግ ምን እንዳስታወሰችኝ ታውቃላችሁ? የገጣሚ ኑረዲን ዒሳን “እኔ ምን አገባኝ” የምትል ግጥም!
እኔ ምን አገባኝ የምትሉት ሃረግ
እሱ ነው ሃገሬን ያረዳት እንደበግ
የሚል ግጥም ልፅፍ
ብድግ አልኩኝና
ምን አገባኝ ብዬ
ቁጭ አልኩ እንደገና፡፡
እኔ ግን በአገር ጉዳይ ምን አገባኝ ብሎ መቀመጥ አልፈጠረብኝም (ዕድል ይሆን ፍርጃ?) በነገራችሁ ላይ መቼና የት እንደሆነ ባላስታውስም የተከበሩ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ፣“በአገራችሁ ጉዳይ ምን አገባኝ አትበሉ!” የሚል ምክር የለገሱ መሰለኝ፡፡ አሁን እንግዲህ በርዕሴ ላይ እንደጠቆምኩት “ጠ/ሚኒስትሩን አነጋገርኳቸው!” ያልኩትን ጉዳይ ላብራራላችሁ፡፡
እውነቴን ነው የምላችሁ አዲሱ ጠ/ሚኒስትራችን (ግን ለምንድነው ሁሌ አዲስ የሚመስሉኝ?) የተከበሩ አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ እንደ ቱባ ባለሥልጣን (ያውም የአገር መሪ!) ፈፅሞ አይከብዱም፡፡ ፊታቸው ላይ የወዳጅነትና የፍቅር መንፈስ እንጂ የመጠራጠርና የተዓብዮ ስሜት አይታይባቸውም (ዓይኔ ይሆን እንዴ?) በእርግጥ ከዚህ ቀደም ከኢቴቪና ከአዲስ አበባ መስተዳድር ቴሌቪዥን ጋር ያደረጉትን ኢንተርቪው ስከታተል ተመሳሳይ ስሜት ተሰምቶኝ ነበር፡፡ በአጭሩ ምን ለማለት ፈልጌ መሰላችሁ? ባለሥልጣን ባለሥልጣን ሳይሆን ሰው ሰው የሚሸቱ ጠ/ሚኒስትር ሆኑብኝ ልል ፈልጌ ነው (ማን ይሆን “ሰዓሊ ከመሆንህ በፊት ሰው ነህ” ያለው?) ለምን እንደሆነ ባላውቅም ጠ/ሚኒስትሩ “ትንሽ ቆይተው----ሥልጣን ሲጥማቸው ይለወጣሉ” የሚል አጉል ጥርጣሬ አደረብኝ፡፡ የብዙ አፍሪካ አገራት መሪዎችን ታሪክ ስላነበብኩ ይሆን? (“before and after power” ታሪካቸውን ማለቴ ነው!) የአፍሪካ አምባገነን መሪዎችማ ቀላል ይለወጣሉ መሠላችሁ! (የሆሊውድ ፊልም ላይ እንዳለችው “ማያ” እኮ ነው እየተቀያየሩ ህዝባቸውን ግራ የሚያጋቡት - አንዴ ሰው ሌላ ጊዜ ወፍ፣ አንዴ ጉንዳን ሌላ ጊዜ ደግሞ ድመት እየሆኑ!) ብቻ አንድዬ ይጠብቀን!!
ፕሬዚዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር በቅርቡ ባደረጉት ልዩ ቃለምልልስ፣ “ከአሁኑና ከንጉሱ ዘመን የፓርላማ ሥርዓት ይበልጥ ነፃነት የሰፈነበት የትኛው ነው?” ሲባሉ፣ ሁለቱ ፓርላማዎች ለየቅል መሆናቸውን ገልፀው፣የአሁኑ “የፓርቲ ዲሲፕሊን” የሚባል ነገር ስላለ ለግለሰቡ “ፍፁም ነፃነት” የሚሰጥ አይደለም ብለዋል (የዲፕሎማሲ ችሎታቸውን ለአንዳንድ የኢህአዴግ አመራሮች ተመኘሁላቸው!) እናላችሁ----ይሄ “የፓርቲ ዲሲፕሊን” የሚሉት ክፉ አባዜ፣እኚህን “ሰው ሰው የሚሸቱ ጠ/ሚኒስትር” እንዳይለውጥብን ክፉኛ ሰጋሁ፡፡ (ፓርቲው የጠ/ሚኒስትርነት “ኩፍጥና” ያንሳቸዋል ብሎ ከገመገማቸው እኮ አለቀልን!)
እኔና እሳቸው በተገናኘንባት የጠ/ሚኒስትር የማትመስል ትንሽዬ ቢሮ ውስጥ ስንታይ፣ አንድ የአገር መሪና ዘወትር ከስጋት ተላቅቆ በማያውቅ የግል ፕሬስ ውስጥ የሚባትል ጋዜጠኛ አንመስልም ነበር፡፡ አስተማሪና ተማሪ እንጂ! በነገራችሁ ላይ የእንግሊዝኛ ጋዜጦቻችን አዲሱን ጠ/ሚኒስትር “ኃይሌ” በሚል አሳጥረው እንደሚጠሯቸው ያወቅሁት በቅርቡ ነው፡፡ እንግዲህ ዝርዝሩን ባላውቅም ከሳቸው ጋር የተገናኘሁት ከግል ፕሬስ ኢንተርቪው ለማድረግ “እጣ ወጥቶልኝ” እንደሆነ የሰማሁት ከአለቃዬ ነው፡፡ (“የፕሬስ ነፃነት በእጣ” የተባለ አይመስልም?) ከሁሉም ያልገባኝ ግን ምን መሰላችሁ? ለምን “አርነት የወጡ ሃሳቦች” የምትል ሚጢጢዬ የግጥም መፅሃፍ በእጄ እንደያዝኩ ነው፡፡ በእርግጥ ገጣሚውን ዳዊት ፀጋዬን በደንብ አውቀዋለሁ፡፡ የግጥሙን መፅሃፍም ፈርሞበት ነው ያበረከተልኝ፡፡ (ኢንተርቪው እንጂ የ“አርነት” ጥያቄ አቅርብ አልተባልኩ!) አልፎ አልፎ ፊትለፊቴ የተቀመጡትን ጠ/ሚኒስትር እየቃኘሁ፣በአብዛኛው ግን ግጥሞቹን ያለቀልቤ እያነበብኩ ሳለ ነው፣ ፕሮቶኮሏ ኢንተርቪውን እንድጀምር ምልክት የሰጠችኝ፡፡ በደመነፍስ መፅሃፍዋን ገልጬ “ለአንተ ስል”
የምትለዋን የዳዊት ግጥም ፈቃዳቸውን ሳልጠይቅ ላነብላቸው ተዘጋጀሁ (ምን ፈልጌ እንደሆነ ግን ለራሴም አልገባኝ!)ንባብ ከመጀመሬ በፊት ቀና ብዬ የጠ/ሚኒስትሩን በመነፅር የተከለሉ ዓይኖች ቃኘት አደረግሁ - የደስታ ብርሃን ይረጫሉ፡፡ ቢያንስ ግጥም እንደማይጠሉ ገባኝ (በሆዴ“አቦ ይመችዎት!” ያልኩኝ መሰለኝ)
ሰዎች በረሃብ ሲያልቁ
አፋቸውን በአንተ እንዳያላቅቁ
ፍትህ በምድር ሲጠፋ
ብስጭታቸው እንዳይከፋ
እምነታቸው እንዳይላላ
ነፍሳቸው አንተን እንዳትጠላ፣
“እግዚአብሄር የለም እንዴ?” ሲሉ
“አዎ የለም” የምለው
ስለ አንተ ብዬ ነው፡፡
ቀና ብዬ ሳያቸው መሳቅ ፈልገው ራሳቸውን የገደቡ ዓይነት ስሜት አነበብኩባቸው - ገፅታቸው ላይ፡፡ ግን ለምን በነፃነት አልሳቁም? (ሺ ዓመት አይኖር!) ትዝ ይላችኋል---- የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር (ነፍሳቸውን ይማረውና!) በሚሊኒየም በዓል ላይ ሚሊኒየም አዳራሽ ውስጥ ከባለቤታቸው ጋር በሱዳንኛ ዘፈን ሲደንሱ? ለምን እንደሆነ አላውቅም፣የዛን ዕለት ደስ ብሎኝ ነበር፡፡ ለጠ/ሚኒስትሩ ሌላ ግጥም ልደግምላቸው ከጅሎኝ ነበር፡፡ (ነፍሴ first thing first ያለችኝ መሰለኝ) በእርግጥ እሳቸውም ሁለተኛ ግጥም እንዲነበብላቸው የፈለጉ ይመስላሉ፡፡ (ጥያቄው በግጥም ንባብ እንዲቀየርላቸው ተመኝተው ይሆን እንዴ?) እውነት ለመናገር ግን በደስታ ስሜት ተጥለቅልቄ ነበር! (ግጥም ይወዳሉ ማለት ነው አልኩ - ለራሴ እየደጋገምኩ!) ግን ለምን ደስ አለኝ? “ግጥም መውደድና አለመውደድ ከባለሥልጣን ሥራና ባህርይ ጋር የሚያገናኘው ነገር የለም” የሚል ሃሳብ ድንገት ወደአዕምሮዬ መጣብኝና ደስታዬን ከመቅፅበት ነጠቀኝ- ምቀኛ! ሃሳቡ እንኳን ስህተት ያለው አይመስልም፡፡ አምባገነን መሪ ምን ግጥም ቢወድ እኮ ከአምባገነንነቱ ላይ አይቀንስለትም! (ግጥም ሰብዓዊነት ያላብሳል ያለው ማነው?) ለነገሩ ከኢህአዴግም ከተቃዋሚዎችም ስንት ባለቅኔ ፖለቲከኞች እኮ አይተናል፡፡ (ቅኔ መቀኘትና ዲሞክራሲን መቀኘት ግን ለየቅል ናቸው!)
ለአይን መግለጫ ያህል አንዷ ግጥም በቂ እንደሆነች በማሰብ በቀጥታ ወደ ጥያቄዎቼ ለመግባት ወሰንኩ፡፡

እሳቸውም ፈተና እንደሚጠባበቅ ትጉህ ተማሪ በትኩረት እየተጠባበቁኝ ነበር፡፡ ለነገሩ የ87 ሚ. ህዝብ ህልቆ መሳፍርት ጥያቄዎችን መመለስ ከየትኛውም ምድራዊ ፈተና የበለጠ ሊከብድ እንደሚችል ለማወቅ “ኒዩክለር ሳይንስ ማጥናት” አይጠይቅም፡፡ በተለይ ከድህነት ለመላቀቅ መከራዋን በመብላት ላይ ያለች ምስኪን አገር የመምራት ሃላፊነት ድንገት ትከሻው ላይ ለወደቀበት “የዩኒቨርስቲ ምሁር”!!
ከጃኬቴ ኪስ ውስጥ ያወጣሁትን ማስታወሻ ደብተር ገልጬ፣ጠ/ሚኒስትሩ በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ ባሉ ቁጥር “የመለስን ራዕይ እናሳካለን” በማለት እንደፀሎት የሚደጋግሙትን ትክት ያለ ንግግር የተመለከተ ጥያቄዬን በማስቀደም ቃለምልልሱን አሃዱ ልል ወደድኩ፡፡
ክቡር ጠ/ሚኒስትር፤አንዳንድ የህብረተሰብ ወገኖች ጠ/ሚኒስትሩ ትክክለኛ ራሳቸውን ሆነው የምናያቸው መቼ ነው ሲሉ ይደመጣሉ (ጠ/ሚኒስትሩ አምልጧቸው ሳቅ አሉ) እውነቴ ነው ጠ/ሚኒስትር… ሁልጊዜ ሲናገሩ የቀድሞውን ጠ/ሚኒስትር ንግግር ከማስታወስና “የመለስን ሌጋሲ እናስቀጥላለን!” ከማለት ውጭ የራስዎትን አቋም የሚያንፀባርቅ ነገር ተናግረው አያውቁም፡፡ እንደውም ዳያስፖራ ያሉ ተቃዋሚዎች፤የምዕራቡ ዓለም “ጐስት ራይተር” ሲሉ ሰምታ ኢትዮጵያም “ጐስት ፕራይም ሚኒስትር” ፈጠረች እያሉ እንደሚቀልዱ ሰምቻለሁ… በዚህ ጉዳይ ላይ ማብራርያ ቢሰጡ ጥሩ ይመስለኛል…
(ጠ/ሚኒስትሩ እንደገመትኩት የስሜት ለውጥ አላሳዩም፤ ዘና ብለው መመለስ ጀመሩ፤ጥያቄዬ ቀድሞ ደርሷቸው ይሆን እንዴ? አልኩ - ለራሴ፡፡ ግን እንዴት ሆኖ? ወዲያው ትኩረቴን ወደመልሳቸው አደረኩኝ) ማንም ምንም ቢል የሚለወጥ ነገር የለም፡፡ አሁንም ወደፊትም የመለስን ሌጋሲ ነው የምናስቀጥለው፡፡ ፓርቲው ለዚህ ትግል ሲመርጠኝ የመለስንና የፓርቲያችንን ራዕይ ከጓዶቼ ጋር ሆኜ እውን ለማድረግ ነው ቃል የገባሁት፡፡ ከዚህ የበለጠም ሆነ ከዚህ ያነሰ አይደለም የእኔ ሚና፡፡ የአገርና የፓርቲ ራዕይ ግለሰቦች በተቀያየሩ ቁጥር የሚቀያየር አይደለም፡፡ ጉዳዩን በዚህ መልኩ ብናየው ሳይሻል አይቀርም (እንዴ---በየት መልኩ?) (ቀጣዩን ጥያቄ አስከተልኩ) በቅርቡ “ጅሃዳዊ ሐልካት” የተሰኘ በአክራሪነት ዙርያ ያጠነጠነ ዶክመንታሪ በኢቴቪ ሲሰራጭ እንኳን፣የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር ንግግር ነው የተደመጠው፡፡ ይሄ ደግሞ በህብረተሰቡ ዘንድ ብዥታ ፈጥሯል፡፡ ይሄን ብዥታ ማጥራት የሚገባ አይመስልዎትም?
ምንም ብዥታ የለም፣ ሁሉም ነገር ጥርት ያለ ነው፡፡ በሁሉም ረገድ ሌጋሲውን የማስቀጠል ዓላማ ይዤ ነው የምንቀሳቀሰው፡፡ ፓርቲውም ለትግል ያጨኝ ይህን አደራ እንድወጣ ብቻ ነው (መልሳቸውን በአጭሩ ገቱት)
አሁን ደግሞ ወደ ተቃዋሚዎች እናምራ -------- ራሳቸውን ከምርጫው ያገለሉ 28 ተቃዋሚ ፓርቲዎች ህዝባዊ ስብሰባ ለማድረግ ፈቃድ አግኝተው፣15 ሆቴሎች አዳራሽ አናከራይም በማለታቸው የምንሰበሰብበት አጥተናል የሚል ቅሬታ ማቅረባቸውን ሳይሰሙ የቀሩ አይመስለኝም------
(ቅንነት የጎደላት የምትመስል ፈገግታ ብልጭ አደረጉና መናገር ጀመሩ) ቅሬታውን እንኳ አልሰማሁትም… እኔ የማውቀው የማተምያ ቤቶቹን ብቻ ነው፡፡ እሱን አንተም እንደምታውቀው፣ነፃ አገር ውስጥ እንደምንኖርና ማንኛውም ባለስልጣን ቢሆን ማተምያ ቤት ደውሎ የ“አንድነት” ጋዜጣን አታትሙ የማለት መብት እንደሌለው ገልጬ፣ነገሩ በዚያው ተቋጭቷል፡፡ የአዳራሹን እንኳን ይሄው ካንተ መስማቴ ነው፡ክቡር ጠ/ሚኒስትር፤ የማተምያ ቤቶቹ ችግር እኮ እርስዎ እንደሚሉት አልተቋጨም፡፡ አንድነት ፓርቲ እንደውም የራሱን ማተምያ ቤት ለማቋቋም የገንዘብ ማሰባሰብያ (Fundraising) ፕሮግራም ሰሞኑን ማዘጋጀት ጀምሯል፡፡
ኤክሰለንት! ፓርቲዎቻችን እንዲህ ችግር ፈቺ ነው መሆን ያለባቸው፡፡ ኢህአዴግም ሊያግዛቸው ይችላል፡፡ ያው ለአገሪቱ የመድበለ ፓርቲ ስርአት መጠናከር አነሰም በዛም አስተዋፅኦ እንዳላቸው ፓርቲያችን ያምናል፣ ስለዚህ ነገሩን የዲሞክራሲ ሥርዓትን እንደማጎልበት በመቁጠር የማተምያ ማሽኑ ከቀረጥ ነፃ እንዲገባ እናግዛቸዋለን፡፡
(ጆሮዬ የሚሰማውን ማመን አቃተው) ይሄ ደስ የሚል ሃሳብ ነው ጠ/ሚኒስትር--- ገዢው ፓርቲና ተቃዋሚዎች በትብብር ቢሰሩ እኮ ጥቅሙ ለአገር ነው… (ሆኖም አላስጨረሱኝም) በትብብር መስራት የሚለው እንኳ አያስኬድም፡፡ የኢህአዴግና የተቃዋሚው መስመር ፈፅሞ የሚገናኝ አይደለም፡፡ ጉዞአችን ለየቅል ነው፡፡ ኢህአዴግ የጠራ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ አቅጣጫን ነው የሚከተለው፡፡ በዚህ ሂደት ደሞ ኪራይ ሰብሳቢዎችን በየጣቢያው እያራገፈ፣ ልማታዊ ኃይሎችን አቅፎና ደግፎ ነው ወደ ግቡ የሚደርሰው፡፡ ስለዚህ ከተቃዋሚዎች ጋር የሚያስተባብረን የጋራ ዓላማ የለንም፡፡ በመርህ ደረጃ ግን ህዝቡ አማራጭ እንዳያጣ የተቃዋሚዎችን መኖር እንደግፋለን (ኢህአዴግን ያመነ አልኩ - በሆዴ!) እሺ የሆቴል መሰብሰቢያ አዳራሽ አጣን ለሚሉት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ምን መፍትሄ ይሰጧቸዋል? (በተስፋ መቁረጥ ስሜት ነው የጠየቅኋቸው)
ዌል… ኢህአዴግ እንግዲህ ሆቴልም አዳራሽም የለውም፡፡ ምናልባት እነ መድረክ እንደ ጦር የፈሩትን የምርጫ ስነምግባር ደንቡን ለመፈረም ፈቃደኛ ከሆኑ፣ በፓርቲዎች የጋራ ምክክር መድረክ በጉዳዩ ላይ ተወያይተን መፍትሄ ልንፈልግለት እንችላለን ብዬ አስባለሁ፡፡
ክቡር ጠ/ሚኒስትር፤ ፓርቲዎቹ እኮ ከህዝብ ጋር መገናኘት አልቻልንም… ሆቴሎች በአድማ አናከራይም ብለውናል… እንደውም የመንግሥት እጅ አለበት እያሉ ነው…
አሁንም ስለማተምያ ቤቶች ስናገር ያልኩትን እደግመዋለሁ፡፡ እኛ ሆቴሎችን እየዞርን “ለመድረክ ፓርቲ አዳራሽ አከራዩ አታከራዩ” እያልን እጃቸውን መጠምዘዝ አንችልም፡፡ መብትም የለንም፡፡ ዲሞክራሲያዊ አገር ውስጥ እኮ ነው ያለነው፡፡ ግን ፓርቲዎቹ፤ “እነዚህ ሁሉ ሆቴሎቹ ለምን እንደ ጭራቅ ፈሩን?” ብለው ራሳቸውን መጠየቅ ያለባቸው ይመስለኛል፡፡ ቆይ ለምን ፈሯቸው? እኔ የተቃዋሚ አመራር ብሆን ኖሮ ምክንያቱን ለማስጠናት እሞክር ነበር… ይሄ እኮ ስር የሰደደ ችግር ነው፡፡ ኢህአዴግ ለምሳሌ እንኳንስ የሆቴል አዳራሽ ኪራይ ሊከለከል ቀርቶ፤“የህዝብ ፓርቲ ስለሆነ ክፍያ አንቀበልም” በሚሉ የሆቴል ባለቤቶች ነው የተቸገረው፡፡ በርካታ አዳዲስ ባለአምስት ኮከብ ሆቴሎች አዳራሻቸውን በነፃ እንድንጠቀም እየጎተጎቱን ነው፡፡
ክቡር ጠ/ሚኒስትር፤ ስልጣን ላይ ያለ ፓርቲና ተቃዋሚ አንድ ሊሆን አይችልም--ተቃዋሚዎች እንደሚሉት፤ በ97 ምርጫ የግል ባለሃብት በሆኑ ደጋፊዎቻቸው ላይ መንግስት በፈፀመው ማስፈራሪያና ወከባ ባለሃብቶች በግልፅ ተቃዋሚዎችን ለመደገፍና ለማገዝ ይፈራሉ ይባላል፡፡ ይሄ ችግር እንዴት ይፈታል ብለው ያስባሉ?
መፍትሄው አንድ ብቻ ነው፤ተቃዋሚዎች እንደ ኢህአዴግ ህዝባዊ ፓርቲ መሆን አለባቸው፡፡ ኢህአዴግ የማተምያ ቤትና የስብሰባ አዳራሽ ችግር የማይገጥመው ገዢ ፓርቲ በመሆኑ አይደለም፤ ሰፊ ህዝባዊ መሰረት ያለው ልማታዊ ፓርቲ ስለሆነ ነው፡፡ (በዚህ ጉዳይ ላይ ከኢህአዴግ ጋር ሙግት መግጠም ጊዜ ማባከን ስለመሰለኝ አንድ ሁለት ከምርጫ ጋር የተገናኙ ጥያቄዎች ላቀርብላቸው ወሰንኩ)
…በሚያዝያ ወር ከሚካሄደው የአዲስ አበባና አካባቢ ምርጫ ጋር በተገናኘ የኢህአዴግ ፅ/ቤት ሃላፊ የሆኑት አቶ ሬድዋን ሰይድ “ተቃዋሚዎች ቢኖሩም ባይኖሩም ትርፍም ኪሳራም የላቸውም” ሲሉ በመናገራቸው በተቃዋሚዎች ጎራ ከፍተኛ ቁጣና ቅሬታ ቀስቅሷል፡፡

የሞባይሌ ድንገተኛ ጩኸት ከተቀመጥኩበት አስፈንጥሮ ሊያስነሳኝ ምንም አልቀረውም ነበር፡፡ በዚያ ላይ ሞባይሉ የትኛው ኪሴ ውስጥ እንደተሰወረ አላውቅም፤አጣሁት - ግን ጩኸቱን ቀጥሏል፡፡ ኪሴዬን በርብሬ በርብሬ ቀና ስል ጠ/ሚኒስትሩ የሉም፡፡ እሳቸው ብቻ ሳይሆኑ መቀመጫቸውም የለም፡፡ እኔና እሳቸው የነበርንበት ጠባብ ቢሮም ራሱ የለም፡፡ እኔም ያለሁት ወንበር ላይ ሳይሆን አልጋዬ ላይ ነኝ - መኝታ ክፍሌ ውስጥ! ሁለተኛውን ትራስ “አርነት የወጡ ሃሳቦች” የምትለዋ የግጥም መፅሃፍ የተንተራሰች መስላ ተቀምጣለች፡፡ ከግል ፕሬሶች መካከል “ዕጣ ደርሶኝ” ጠ/ሚኒስትሩን ኢንተርቪው ላደርጋቸው ቢሮአቸው መግባቴ በእውኔ ሳይሆን በህልሜ እንደነበር የተገነዘብኩት ዘግይቼ ነው፡፡ ከጠ/ሚኒስትሩ ጋር በህልሜ የጀመርኩትን ቃለምልልስ ሳልጨርስ ከመባነኔ የበለጠ ያናደደኝ ግን ላነብላቸው ያሰብኩትን ወሳኝ ግጥም ባለማንበቤ ነው፡፡ በህልምም ቢሆን ባነብላቸው ይሻል ነበር ብዬ ተፀፀትኩ፡፡ ከዚያም መፅሃፊቱን ጐተት አድርጌ እንደዘበት ገለጥ አደረግኋት - ልክ የታዘዘ ይመስል ገፅ 35 ለእሳቸው ያሰብኩት ግጥም ላይ አረፍኩ - “ህዝብ፣ እግዜር፣ መንግስት!” ይላል ርእሱ፡፡
እግዚአብሄር፣
ምን ብሎ ይመልስ የህዝብን እሮሮ?
መንግስትን፣
እንዲናገር እንጂ እንዳይሰማ ፈጥሮ!
ጠ/ሚኒስትሩ እቺን ግጥም ቢሰሙ ምን አይነት ስሜት ይፈጠርባቸው ይሆን? (በህልም አለምም ቢሆን ማለቴ ነው!)

  • የኢትዮጵያ ቡድን ድንገት ወደ አፍሪካ ዋንጫ ብቅ ሲል፣ በሆይሆይታና በትኩሳት ተውጠን ዋንጫውን ተሸክመው የሚመጡ መስሎን አልነበር?
  • በፖለቲካና በኢኮኖሚ በኩልም መንግስት ሆይሆይታ ላይ ነው - የመሻሻል ጭላንጭል አየሁ ብሎ አገሪቱ የአለም አንደኛ የሆነች ያስመስላል። 
  • ከአምስት አመት በፊት፤ ኢትዮጵያ በፖለቲካም ሆነ በኢኮኖሚ የቱን ያህል የእልቂትና የመበታተን አደጋ ውስጥ እንደሆነች፣ ገደል አፋፍ ላይ እንደቆመች መንግስትና ኢህአዴግ ሲነግሩን ነበር - ያለ ኢህአዴግ ትበታተናለች እያሉ። 
  • የኢቴቪ ዜናና ዘገባዎችን የሚመለከት ሰው፤ ገበሬዎች በሃብት የተጥለቀለቁ ይመስለዋል - በመስኖ፣ በምርጥ ዘር፣ በቴክኖሎጂ። ከአምስት አመት በፊት እንደነበረው ዛሬም 12 ሚሊዮን ገበሬዎች በእርዳታ የሚተዳደሩ ናቸው። 
  • የባለስልጣናትን ሪፖርት የሚያደምጥ ሰው፤ ለወጣቶች የስራ እድል የተትረፈረፈ ይመስለዋል - በሁለት አመት በከተሞች ውስጥ ከ1.5 ሚ በላይ የስራ እድሎች ተከፍተዋል ስለተባለ። ግን አምና የተፈጠረው ስራ ዘንድሮ የለም።

 ሃሳብና ስሜት፣ “በልኩ ካልሆነ” ... ማለትም ከእውኑ ሃቅ ጋር ካልገጠመ፤ “ከእውነት የራቀ ስህተት” ይሆናል። “ልክ ሲያጣ” ደግሞ፤ “ጭፍንነት” ይባላል። ሲብስበትስ? ሃሳብና ስሜት ከእውኑ ተፈጥሮ ጋር ዝምድናው ጨርሶ ሲሰረዝስ? ያኔ አእምሮ ተቃውሷል ማለት ነው። ኢትዮጵያም ይሄውና እንደተቃወሰች ሺ አመታት ተቆጥረዋል። ህመሟ ምንድነው በሉኝ። ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሰ የጭፍንነት በሽታ ነው የሚያሰቃያት - ስር የሰደደ “ልክ የማጣት” በሽታ! ሁለት የበሽታ ምልክቶች ሲፈራረቁባት አታዩም? ብዙውን ጊዜ ብርድ ብርድ ይላታል። ሌላ ጊዜ ደግሞ በትኩሳት ያነድዳታል። በ60ዎቹ ዓ.ም እንዲሁም በ97ቱ ምርጫ የተግለበለቡትን ትኩሳቶች አስታውሱ። በየመሃሉ የነገሱትንና አሁን የሰፈነውን የፖለቲካ ድንዛዜም ተመልከቱ። 

በእግር ኳስም ተመሳሳይ የትኩሳትና የድንዛዜ ምልክቶች በብዙዎች ላይ ተፈራርቀዋል። የእግር ኳስ ስሜት ከጣራ በላይ ሲንበለበል እንደነበር ለማወቅ ብዙ መመራመር አያሻም፤ ይድነቃቸው ተሰማ ለዘመናት ዝነኛ ሆነው የዘለቁት ለምን ሆነና? ግን ትኩሳቱ ቦታውን ለቅዝቃዜ መልቀቁ አልቀረለትም። ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ዋንጫ ተራራቀች። ለሰላሳ አመት የዘለቀውን ልክ ያጣ የተስፋ መቁረጥ ድንዛዜን፤ ዘንድሮ ከተንቀለቀለው የስሜት ጡዘት ጋር አጣምራችሁ ተመልከቱት። አገሪቱ ላይ ለሺ ዘመናት የተፈራረቁት ሁለት የበሽታ ምልክቶች፤ ዛሬም አልተለይዋትም።
ታዲያ “አገር ታመመች፣ ኢትዮጵያ ተሰቃየች” ሲባል፤ ምሳሌያዊ አነጋገር እንደሆነ አትዘንጉ። በምሳሌያዊ አነጋገር ታጭቀን እያደግን፤ “አገር” የሚባለው ነገር፤ ከምር አካልና ህይወት ያለው ፍጡር እየመሰለን ብዙ ጥፋት ደርሷል። “ለራስህ ጥቅም ሳታስብ ለአገርህ ሙትላት!”፣ “ከራስህ በፊት የአገርህን ጥቅም አስቀድም! ኢትዮጵያ ትቅደም” እየተባለ ስንት ሰው አልቋል። እናም... ለሺ አመት የታመመች አገር ሁለት የበሽታ ምልክቶች ይፈራረቁባታል ያልኩት፤ ባለፉት ሺ አመታት አብዛኞቹ ኢትዮጵያዊያን በአመዛኙ በምን አይነት ሕይወት እንዳለፉ ለመግለፅ ነው።
“ልክ የማጣት” ወይም የጭፍንነት አባዜ ያልለቀቃቸው ብዙ ኢትዮጰያውያን፣ ከስኬት ርቀው በውድቀት ውስጥ ተሰቃይተዋል ለማለት ነው የፈለግሁት። ብርድ ብርድ እያላቸው ሲኮራመቱና እያሰለሰ ትኩሳት ሲያንገበግባቸው ስንት ዘመናቸው! አንዳንዴ፤ “ውድቀት መፍትሄ የሌለው የእጣፈንታ ወይም የእርግማን ሸክም ነው” በሚል ልክ ያጣ የተስፋ መቁረጥ ስሜት አገሪቱን እየወረራት፤ በድንዛዜ የመኮራመት አባዜ ይነግስባታል። ትንሽ ቆይቶ ደግሞ፣ ስኬትና ለውጥ፣ እድገትና ድል በአንዳች ልዩ “ተአምር” የሚገኝ ትንግርት ይመስል፤ ልክ ያጣ የስሜት ትኩሳትና የሆይሆይታ ማዕበል ያጥለቀልቃታል። ትንሽ የመሻሻል ጭላንጭል ብልጭ ጎላ ብላ ከወጣች፤ በቃ... አገር ይቀወጣል።
ትንሽ የኢኮኖሚ መነቃቃት ብልጭ ስላለች፣ መንግስት የሚያደርገውን ሲያሳጣው አትመለከቱም? አገሪቱ፣ የኬንያውያን የኑሮ ደረጃ ላይ ለመድረስ ገና አስር አመት የሚያስፈልጋት ቢሆንም፤ ኢቴቪን በየእለቱ የሚከታተል ሰው ግን ኢትዮጵያ የአለም ቁንጮ የሆነች ሊመስለው ይችላል። ያው፤ የኢትዮጵያ መንግስትና የመንግስት ጋዜጠኞችኮ ከሌላ ፕላኔት የመጡ አይደሉም፤ እንደ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ድንዛዜና ትኩሳት ይፈራረቅባቸዋል። አሁን የትኩሳት ፈረቃ ላይ ናቸው። እንደ እግር ኳሱ ሆይሆይታ ማለት ነው። ግን አይዘልቅም። በአንዳች ተአምር እውን እንዲሆን የሚጠብቁት የስኬት ውጤት፤ በጭፍን ስሜት እየተግለበለቡ የሰበኩለት ልዩ “ትንግርት” የውሃ ሽታ ሆኖ ሲቀርስ? ስኬትና እድገት፣ በአንዳች ተአምር እውን አይሆንማ።

ያኔ፤ አገሪቱ እንደገና ተመልሳ ወደ ተስፋ ቢስነትና ወደ ድንዛዜ እየተንሸራተተች ትገባለች። እንዲህ ሁለት የበሽታ ምልክቶች እየተፈራረቁ በዥዋዥዌና በአዙሪት ስንት ዘመን ተቆጠረ? ደግሞምኮ፤ “ልክ የማጣት” የጭፍንነት ህመምን ብቻ ሳይሆን ሁለቱ የበሽታው ምልክቶቹን በጣም ስለተላመድናቸው ለብዙ ሰዎች እንደ “ኖርማል” የሚቆጠሩ ሆነዋል። እስቲ የፖለቲካውና የኢኮኖሚውን ነገር ከማየታችን በፊት የእግር ኳሱን ዡዋዥዌና አዙሪት ትንሽ እንየው።
“ባርሴሎናን ያስናቀ ቡድን”
የኢትዮጵያ የእግር ኳስ ቡድን ከ30 አመት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ሲገባ፣ ትንሽ የለውጥ ፍንጭ መሆኑ አይካድም። ታዲያ በዚህ ትንሽ የመሻሻል ጭላንጭል ተደስተን፤ ምንጩንና ምክንያቱን ለይተን ለማወቅና ይበልጥ የሚያድግበትን መንገድ ለመፍጠር ብርታት አገኘን? ማለትም በደንብ ለማሰብ ተነቃቃን? ጥያቄው ራሱ “ይደብራል” - ለብዙ ሰዎች። በእርግጥ፣ ብዙ ሰው “በደንብ ለማሰብ” ባይነቃቃም፤ በሆነ መልኩ ተነቃቅቷል። እንዲያውም፣ ከአፍሪካ ዋንጫ ጋር ተያይዞ ለተወሰነ ጊዜ፤ “የህዝብ ንቅናቄ ተቀጣጥሏል” ማለት ይቻላል (በዘመኑ የፖለቲካ ቋንቋ እንናገር ከተባለ)። የቢሮ ውስጥና የድራፍት ላይ ወሬው፣ የራዲዮና የጋዜጣ ዘገባው በብርሃን ፍጥነት እንደ ሰደድ እሳት አገር ምድሩን ሲያንቦገቡገው ማየት ያስደንቃል።
የብሄራዊ ቡድን አባላትን ለመሸለም፣ ከየአቅጣጫው ይሰበሰባል የተባለው ገንዘብስ ቀላል ነው እንዴ? በስፖርት ውድድሮች አውራ (በአለማቀፉ የኦሎምፒክ መድረክ) የወርቅ ሜዳሊያ ያጠለቁ ኢትዮጵያዊያን ሻምፒዮኖች ከ100ሺ ብር በላይ እንዳልተሸለሙ አትርሱ። የእግር ኳስ ቡድንኑ በአፍሪካ ዋንጫ “ከቀናው” ግን፣ እያንዳንዱ ተጫዋች ሁለት ሚሊዮን ብር ገደማ ሽልማት እንዲያገኝ ከ60 ሚሊዮን ብር በላይ ገንዘብ ይሰበሰባል መባሉ ራሱ...፣ “የህዝብ ንቅናቄ ተቀጣጠለ፤ የእግር ኳስ ሰራዊት ተነቃነቀ” የሚያስብል ነው። በእርግጥ፤ በወቅቱ ጥርጣሬ የገባቸው ሰዎች ጥቂት አይደሉም። ያጠራጠራቸው ነገር ምን እንደሆነ በቀላሉ ልትገምቱት ትችላላችሁ። “ገንዘቡ ተሟልቶ ይሰበሰባል ወይ?” የሚለው ጥያቄ ነበር ያሳሰባቸው።

ብሄራዊ ቡድኑ ለዋንጫ ደርሶ ሻምፒዮን እንደሚሆን እርግጠኛ እስከመሆን ደርሰዋላ።
መጀመሪያ ላይማ፤ ስለ ዋንጫ የሚያስብ ሰው ብዙ አልነበረም። ቡድኑ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ውድድር ለመግባት በመቻሉ ብቻ ብዙዎች ረክተዋል። ግን በውድድሩ የአንደኛ ዙር ጨዋታዎች ላይ ቡድኑ ጥሩ ተፎካካሪ ሊሆን ይችላል? ጥያቄው ወደ ምኞት፣ ከዚያም ወደ እምነት ለመለወጥ ጊዜ አልፈጀበትም። ቡድኑ ወደ ጥሎ ማለፍ እንደሚደርስ ብዙ ሰዎች በስሜት ወደ መናገር የተሸጋገሩት እንዴት እንደሆነ፤ በየት በየት በኩል አጥር ጥሰው እንደዘለሉ ለማስታወስ ያስቸግራል። ግን በዚህ አላበቃም። ቡድኑ ወደ ግማሽ ፍፃሜ ቢያልፍስ? እንዲያው ለግርምት ያህል ሽው ያለው የምኞት ስሜት፣ እንዴት እንደሆነ ሳይታወቅ እግር አብቅሎ መራመድ ይጀምራል።
ገና የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ሳይከፈት፤ ትኩሳት ባነደደው የብዙዎች ስሜታዊ አእምሮ ውስጥ፣ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ግማሽ ፍፃሜውን አልፎ የዋንጫ ፍልሚያ ላይ ደርሷል። አሳሳቢው ነገር፣ ስፖርተኞቹ ዋንጫ ይዘው ሲመጡ፤ ቃል የተገባላቸው ሽልማት ተሟልቶ ይሰጣቸዋል? የሚለው ጥያቄ ነው። “ውድድርና ብቃት” እና “ትኩሳትና ተአምር” እየተቀላቀሉ፣ የቀን ህልምና የቀን ሃሳብ እየተምታቱ፣ “ህዝባዊው ንቅናቄ” ፍጥነቱን እየጨመረ በጥቂት ቀናት ውስጥ ከቁጥጥር ውጭ ሆነ - ያለ ፍሬን እንደሚንደረደር መኪና። ልክና ስፍር አጥቶ በሚጦዝ ስሜት ሆይሆይታው ቀለጠ።
አሰልጣኙና ተጫዋቾቹ፣ በዚህ የስሜት ግልቢያ ውስጥ ተዋናይ ላለመሆን በእጅጉ ቢጠነቀቁም፣ ሆይሆይታውን ሊቋቋሙት አልቻሉም። ተቆጣጣሪ አእምሮ ያጡ ተአምራዊ የትኩሳት ትረካዎች ማቆሚያ አልተገኘላቸውም... “ቡድኑ ዋንጫውን ተሸክሞ ከመጣ... ደግሞም ተሸክሞ ይመጣል። አጨዋወታቸውኮ ባርሴሎናን ያስንቃል። በዚህ አይን ሜሲ ምኑን ተጫወተው?... ቃል የተገባው ሽልማት አያሳስብም። የገንዘቡ በጊዜ ይሰበሰባል። ይልቅስ አስጨናቂው ነገር ሌላ ነው። የኢትዮጵያ ቡድን ለዋንጫ የሚደርሰው ከደቡብ አፍሪካ ጋር ከሆነ፤ ዳኛው ማዳላቱ አይቀርም። በዚያ ላይ የኢትዮጵያ ቡድን አሸንፎ ሲወጣ፣ አደጋ ሊደርስበት ይችላል”... ምን አለፋችሁ፤ አገር በትኩሳት ማዕበል ተናጠች።
በሰላሳ አመታት የውድቀት ታሪክ ስሜቱ ተሽመድምዶ፤ እንደ እጣ ፋንታ ወይም መፍትሄ እንደ ሌለው እርግማን ሸንፈትን ተሸክሞ፣ ሙትት ብሎ የደነዘዘው መንፈስ፤ ትንሽ የመሻሻል ጭላንጭል ሲያይ ምን እንዲሆን ትጠብቃላችሁ? “ለብርቱ ጥረት የሚያነሳሳ ቁጥብ የመነቃቃት መንፈስ” እንዲፈጠር ከጠበቃችሁ ተሳስታችኋል። መነቃቃት ሳይሆን ትኩሳት ነው የተፈጠረው - በሆይሆይታ የቀለጠ ጡዘት። ትንሽዬ የመሻሻል ጭላንጭል ብልጭ ስትል፤ በአንዳች “ተአምር” ብሄራዊው ቡድን የአፍሪካ አንደኛ ሆኖ ቁጭ አለ - በስሜት የተበጠበጠ አእምሯችን ውስጥ። ዋንጫ የሚያስገኝ አንዳች ልዩ “ተአምር”፣ እንደተጠበቀው ከተፍ አለማለቱን ስናይስ? ወደ ቀድሞው ድንዛዜ መመለስ በአገራችን በጣም የተለመደ ባህል ነው።
በፖለቲካና በኢኮኖሚ - ድንዛዜና ትኩሳት
በአገራችን የፖለቲካና የኢኮኖሚ ሁኔታ ውስጥ የምናየው ሁኔታም ከእግር ኳሱ ስሜት ጋር ይመሳሰላል። ለካ፣ መንግስትም የአገሪቱ የኢኮኖሚና የፖለቲካ ህዳሴን ነጋ ጠባ በሚንቀለቀል ፕሮፓጋንዳ የሚጠዘጥዘን፣ ልዩ የማጋነን ሱስና የፕሮፓጋንዳ ጥም ስላለበት አይደለም። ያው እሱም፣ ትናንሽ የመሻሻል ጭላንጭሎችን ሲመለከት፣ እንደ አብዛኞቻችን ናላው እስኪዞር ድረስ በትኩሳት ስለሚንገበገብ ነው። ለአመታት በድንዛዜ ተውጠው የነበሩ በርካታ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎችና አባላትስ በ97ቱ ምርጫ፤ ትኩሳት ነግሶባቸው እንዴት እንዴት እንዳደረጋቸው ታስታውሱ የለ? ያው የመንግስት ባለስልጣናትና የመንግስት ጋዜጠኞች፤ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎችና አባላትኮ እንደ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ናቸው - ድንዛዜና ትኩሳት የሚፈራረቅባቸው። ለዘመናት የተቆራኘን ባህል ነዋ።
ውድቀትን እንደ እርግማን ቆጥሮ፣ ለውጥ እንደማይመጣ አምኖ፣ በተስፋ ቢስነት “የባሰ አታምጣ” እያለ በድንዛዜ ይቀመጣል - በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ፣ በእግር ኳስ። ድንዛዜን ተከናንቦ ሲኮራመት፤ ቢቀሰቀስ እንኳ አይሰማም። ትናንሽ የመሻሻል ጭላንጭሎች ብቅ ብቅ ሲሉ እንኳ ለማየት ፈቃደኛ አይሆንም። ውድቀትን እንደ እርግማን፣ ስኬትን እንደ ተአምር እየቆጠረ ምኑን ያያል! የለውጥ ምንጮችንና የስኬት ስረ መሰረቶችን ለይቶ ለማወቅ ጠንካራ ፍላጎት አይኖረውም። ለዚህም ነው፤ የ97ቱ የተሟሟቀ የምርጫ ውድድር ለብዙ ሰዎች እንደ አንዳች ተአምር የሚሆንባቸው። አለበለዚያማ ከ95 ዓ.ም ጀምሮ፣ በፖለቲካው መስክ የመሻሻል ጭላንጭሎች ብቅ ብቅ ሲሉ ማየት ይቻል ነበር። ተቃዋሚ ፓርቲዎችን የማዋከብ፣ እንዲሁም ምሁራንን የማንቋሸሽና ጋዜጠኞችን የማስፈራራት አፈና እየቀነሰ ነበር። ተቃዋሚ ፓርቲዎችም፣ “ወያኔ” የሚለውን የዘወትር አጠራር እየተዉ፣ ኢህአዴግ ወይም ገዢው ፓርቲ ማለትን የጀመሩት ያኔ ነው።

በ97ቱ ምርጫ ላይ ጎላ ብሎ የታየው የለውጥ ጭላንጭል፤ በአንዳች ተአምር ከሰማይ የወረደ ሳይሆን በጥቃቅን የለውጥ ምንጮች ምክንያት የተከሰተ መሆኑ ብንገነዘብ ኖሮ፤ ብዙ ሰው ወደ ስሜት ትኩሳት ይገባ ነበር?
እነዚህን የመሳሰሉ የፖለቲካ ጥቃቅን የለውጥ ጭላንጭሎች የታዩበት ዘመን፤ በኢኮኖሚም በኩል የለውጥ ፍንጮች ብቅ ብቅ ብለዋል። የቢዝነስ ሰዎችን በጠላትነት ይፈርጅ የነበረው ኢህአዴግ አቋሙን በማለዘብ፣ የኢንቨስትመንት ህጉን ያሻሻለው በ1995 ዓ.ም ነው። የተለያዩ አላስፈላጊ ገደቦችንና ቁጥጥሮችን በተወሰነ ደረጃ ሲሰረዙ፤ በተንዛዛ ቢሮክራሲ ተተብትቦ ለነበረው የንግድ ፈቃድና የኢንቨስትመንት ምዝገባ ትንሽ መፈናፈኛ ይሰጣል። ባለፉት አመታት በአገራችን የታየው የኢኮኖሚ የለውጥ ጭላንጭል፤ በአንዳች ተአምር የተፈጠረ ሳይሆን፤ ከጥቃቅን የለውጥ ምንጮች የፈለቀ እንደሆነ መንግስት ባይዘነጋ ኖሮ፤ አሁን እንደሚታየው በትኩሳት እየነደደ “ያዙኝ ልቀቁኝ” ብሎ ያስቸግር ነበር?
አብዛኛው ሰው የስኬት ዋና ምንጮችን ከስረ መሰረታቸው የመመርመር ዝንባሌ የለውም። በዚያው መጠንም ውድቀት ውስጥ ደንዝዞ፤ ጥቃቅን የመሻሻል ፍንጮችንና ጭላንጭሎችን የማየት ፍላጎት የለውም። የማይጨበጡ የተስፋ መና ይሆኑበታል። ውድቀት እንደሆነ የማይላቀቁት እርግማን ነው ብሎ ለሚያስብ ሰው፤ ማንኛውም ስኬት በየትኛውም አቅጣጫ ከከንቱ ህልም ያለፈ ትርጉም አይኖረም። ታዲያ የመሻሻል ጭላንጭሎችን እያዩ በማያዛልቅ ተስፋ ልብን ማንጠልጠል ምን ዋጋ አለው? ምንጫቸው ምንድነው ብሎ መመርመርስ ምን ጥቅም አለው? ሊያያቸው አይፈልግም። ቢያያቸውም ከቁም ነገርም ሳይቆጥር ያጣጥላቸዋል።
ግን ከዚያስ? የመሻሻል ጭላንጭሎቹ ጎላ ጎላ ሲሉና የለውጥ ምልክቶች መታየት ሲጀምሩስ? ... የአገሪቱ ኢኮኖሚ ለተከታታይ አመታት ከአስር በመቶ በላይ እድገት ሲያስመዘግብ፣ የፓርቲዎች ክርክር በነፃነት ሲሰራጭና የምርጫ ፉክክር ሲሟሟቅ፣ ብሄራዊ ቡድኑ ለአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ሲያልፍስ? ያኔ ብዙ ሰው በአግራሞት እያየ፤ “ተአምር ነው፤ ለማመን ይከብዳል!” ይላል። ቢሆንም “ለማመን ይከብዳል” እያለ፣ ማመን ይጀምራል - በ”ተአምር” ያምናል። የስኬት ምንጮችን ከስረ መሰረታቸው ለይቶ ለማወቅ ፍላጎት ስላልነበረው፤ ማንኛውም አይነት የስኬት ጭላንጭል ሲያጋጥመው፤ “ይሄ በአንዳች ተአምር የተገኘ ውጤት ነው” ብሎ ሊያምን ይችላል። ውድቀት እንደ እርግማን ከሆነበት፤ ስኬት ደግሞ እንደ ትንግርት ይሆንበታል። ከአንድ ስትተት ወደ ሌላ ስህተት እየዘለለ ይገባል። እርግማንን በማመን በድንዛዜ ውስጥ የከረመ ሰው፣ ተአምርን በማመን ከመቅፅበት ወደ ሆይሆይታ ይሻገራል።
በተቃዋሚ ፓርቲዎች ዘንድ፣ ያኔ በ97ቱ የምርጫ ወቅት፣ በአንዳች ምትሃት ለውጥ እንደሚመጣ አምኖ፣ “ዛሬውኑ ገዢውን ፓርቲ አስወግጄ ትንግርታዊ ለውጥ ካላየሁ” የሚል ሆይሆይታ የተፈጠረው በትኩሳት አባዜ ሳቢያ ነው - የስኬትን ምንጭ ካለመገንዘብ ጋር የተያያዘ አባዜ። የስኬትን ምንጭ በአግባቡ የሚገነዘቡ ብዙ ሰዎች ቢኖሩን ኖሮማ፣ ገዢውን ፓርቲ በማስወገድ ተአምራዊ ለውጥ እንደማይመጣ አይጠፋቸውም ነበር። “ስልጡን የፖለቲካ ለውጥ እውን የሚሆነው፤ በአንዳች ተአምር ሳይሆን፣ በረዥም ጊዜ የነፃነት አስተሳሰብን በማስፋፋት ነው” የሚል የስኬት ስረ መሰረት ስላልተገነባ፤ የቀድሞው ድንዛዜ ከመቅፅበት ወደ ትኩሳትና ወደ ሆይሆይታ ተቀየረ። በ2002 ምርጫ 99.9 በመቶ አሸነፍኩ የሚለው ኢህአዴግም እንዲሁ፣ አገሪቱ የእልቂትና የብተና አፋፍ ላይ ነች ሲል እንዳልነበረ፤ ድንገት ተነስቶ የኢትዮጵያ ህዳሴ ተበሰረ እያለ ትንግርታዊ ትረካዎችን ሲያራግብ የሰማነው የጤንነት አይደለም - ትኩሳት ነው። በፈጣን እድገት የአለም አንደኛ ሆኛለሁ ብሎ ተአምራትን እየሰበከ፤ ከ2007 በኋላ የእርዳታ እርዳታ አልፈልግም ብሎ ያውጃል። የትኩሳት ነገር... በቃ፤ የምትናገረውን ያሳጣል። 99.9 በመቶ በማሸነፍም፣ ተቃዋሚዎችን እንዳያንሰራሩ በማንኮታኮት ወይም አገሬውን 1ለ5 አደራጅቶ እለት በእለት የህዝቡን እንቅስቃሴ በመቆጣጠርም፣ የህዳሴ ለውጥ አይመጣም። እንዲያውም ከነባሩ የኢትዮጵያ ባህል ንቅንቅ አለማለታችንን ነው የሚያሳየው። ያለ ተፎካካሪ አገሪቱን ሰጥ ለጥ አድርጎ በብቸኝነት የመግዛት ፍላጎትኮ ለዘመናት የዘለቀ ነባር የኢትዮጵያ ባህል ነው።
በአጭሩ፤ በፖለቲካ በኩል ያየናቸው የለውጥ ጭላንጭሎች፤ በስኬት ስረ መሰረት ላይ የተገነቡ ስላልሆኑ፤ በሆይሆይታ፣ በትኩሳትና በግርግር ውስጥ ብዙም ሳይቆዩ በነባሩ የጥላቻና የመጠፋፋት ረግረግ ተውጠው ይቀራሉ። እናም “ተአምረኛው”፣ “ትንግርታዊው” ለውጥ የውሃ ሽታ ይሆንና፤ ትኩሳቱና ሆይሆይታው ትርጉም ያጣል። ከዚህ ውድቀት ጋር ቀስ በቀስ ድንዛዜ ይነግሳል። “ተወው ባክህ! የኢትዮጵያ ፖለቲካ መቼም አይለወጥም! ከእርግማን አይለይም” የሚል ስሜት የተጫጫነው ሰው ይበዛል። በጭፍንነት ሳቢያ የሚፈጥር አዙሪት ነው - ዡዋዥዌ። ከውድቀት ጋር የእርግማን እምነትና ድንዛዜ ይነግሳል - ዝምታና ቁዘማ የበዛበት ድንዛዜ። ከዚያ ደግሞ ከለውጥ ጭላንጭል ጋር የተአምር እምነትና ትኩሳት ይቀጣጠላል - ሆይሆይታና ግርግር የበዛበት ትኩሳት። ያው ትኩሳትም የጭፍንነት ምልክት ስለሆነ፤ ውጤቱ አያምርም - እንደገና ተመልሶ ወደ ውድቀት፣ ወደ እርግማን እምነትና ወደ ድንዛዜ ይገባል።
የእድገትን ጭላንጭል የሚያዳፍን ሆይሆይታ
የአገሪቱ ኢኮኖሚም እንዲሁ ከተመሳሳይ አዙሪት ወይም ከዡዋዥዌ አላመለጠም። የአገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ የመሻሻል ጭላንጭል ጎላ ብሎ የወጣው የሚሌኒየሙ መባቻ 2000 ዓ.ም በተቃረበበት ወቅት ነው። ያለ ተጨባጭ ምንጭ በአንዳች ተአምር የተከሰተ ጭላንጭል አይደለም። የንግድ ፈቃድና የኢንቨስትመንት ምዝገባ ላይ ከ95 ዓ.ም በኋላ ተግባራዊ በተደረጉ መጠነኛ ማሻሻያዎች አማካኝነት ነው፣ የለውጥ ጭላንጭል ብቅ ያለው። ለአምስት ተከታታይ አመታት ከአስር በመቶ በላይ እድገት ተገኝቷል ተባለ።
ከዚያማ መንግስትን ማን ይቻለው? እድገቱኮ ገና ጭላንጭል ነው። አገሪቱ ገና ከድህነት ፈቀቅ አላለችም። የመጨረሻው የድህነት ጠርዝ ላይ ከሚገኙ አስር የአፍሪካ አገራት መካከል አንዷ ነች። ቢሆንም፤ በዚያችው ጭላንጭል ሆይሆይ ማለት ተጀመረ። መንግስት በስሜት ጦዘ። “ለአፍሪካ በአርአያነት የሚጠቀስ የኢኮኖሚ እድገት ያስመዘገበ ልማታዊ መንግስት” ተብሎ ተዘመረ። መንግስት ይበልጥ ከኢኮኖሚው እንዲወጣና ነፃ ገበያ እንዲስፋፋ ከማድረግ ይልቅ፤ “ኢኮኖሚውን በስፋት የሚቆጣጠር ልማታዊ መንግስትን እናጠናክራለን” የሚሉ መፈክሮች በየአቅጣጫው ተስተጋቡ።
የእድገት ጭላንጭል ለመታየት የበቃው በምን ምክንያት እንደሆነ ተረስቶ፤ መንግስት የአገሪቱን ኢኮኖሚ ከዳር ዳር ለመቆጣጠር ሰፊ ዘመቻ ከፈተ። የ95ቱ ማሻሻያ ተንኮታኩቶ፣ በአላስፈላጊ ቁጥጥሮችና በተንዛዛ ቢሮክራሲ ኢንቨስትመንትን የሚተበትብ አዲስ አሰራር የታወጀው በ2002 ዓ.ም ነው። የአገር ኢኮኖሚ የሚያድገው፤ ሁሉም ሰው የራሱን ሕይወት ለማሻሻል በሚያደርጋቸው የግል ጥረቶች፣ የግል ኢንቨስትመንቶችና የቢዝነስ ስራዎች ሳይሆን፤ በመንግስት ቁጥጥርና ድጎማ ነው ተብሎም፤ በዚያው አመት እቅድ ወጥቷል - የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ።
እቅዱ፤ በአምስት አመት ውስጥ የአገሪቱን ኢኮኖሚ በእጥፍ ለማሳደግ፣ በአነስተኛና ጥቃቅን ተቋማት ለ3 ሚሊዮን ዜጎች ስራ ለመፍጠር፣ የግብርና ምርትን በሃምሳ በመቶ ለማሳደግ፣ ኢንዱስትሪውን በ150% ለማሳደግ ያስችላል ተብሎ ሲወደስ ሰምታችሁ ይሆናል። መቼም ይህን እድገት እውን ለማድረግ ኢንቨስትመንት ያስፈልጋል።

ታዲያ፣ በእቅዱ መሰረት፣ የዜጎች የኢንቨስትመንት ድርሻ 30 በመቶ ገደማ ብቻ ነው። የመንግስት የኢንቨስትመንት ድርሻ ደግሞ 70 በመቶ ገደማ። በሌላ አነጋገር፤ ተአምራዊ እድገት የሚመጣው በመንግስት በኩል ነው።
ለእድገት ጭላንጭል መነሻ የሆኑት መጠነኛ የነፃ ገበያ ማሻሻያዎችን በማፍረስና በተቃራኒው የመንግስትን ቁጥጥር በማሳበጥ እንዴት እድገት ይገኛል? በአንዳች ተአምር? በስሜት የተጥለቀለቀው መንግስት ለእንደዚህ አይነት ጥያቄ ጊዜ አልነበረውም። “እንዲያውም ከአምስት አመት በኋላ የእርዳታ እህል አንፈልግም” ብሎ አወጀ። እንግዲህ ያኔ 12 ሚሊዮን ያህል ተረጂዎች ነበሩ። ዛሬ፣ ከሁለት አመት ተኩል በኋላ፤ የተረጂዎቹ ቁጥር ቀንሷል? በጭራሽ። አሁንም 12 ሚሊዮን ገደማ የገጠር ነዋሪዎች ያለ እርዳታ መኖር አይችሉም። በእቅዱ ላይ እንደሰፈረው፤ ኢንዱስትሪው በ20 በመቶ እያደገ ነው? በጭራሽ። እንደታቀደው፤ የግብርና ምርት በ8.5 በመቶ እያደገ ነው?
የታሰበው ያህል እድገት እየተመዘገ እንዳልሆነ የአለም ገንዘብ ድርጅት በተደጋጋሚ ሲገልፅ ቢቆይም፤ መንግስት ብዙ ዘግይቶ ሰሞኑን እውነታውን በመቀበል ለመጀመሪያ ጊዜ መግለጫ ሰጥቷል። በመግለጫው መሰረትም፤ የ2004 የግብርና ምርት እድገት ወደ 5 በመቶ የሚጠጋ ነው። የስታትስቲክስ ኤጀንሲ የ2005 ዓ.ም የእርሻ ምርት ጥናታዊ ግምት እንደሚያሳየው ደግሞ፤ የዘንድሮውም እድገት ከዚህ የተሻለ አይሆንም። በዚህ ስሌት የግብርና ምርት በሃምሳ በመቶ ለማደግ ዘጠኝ አመት ያስፈልገዋል።
እንደተባለው፤ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ወጣቶች የስራ እድል እያገኙ ነው? ካቻምና ግማሽ ሚሊዮን ወጣቶች፣ አምናም እንዲሁ ግማሽ ሚሊዮን ወጣቶች በአነስተኛና ጥቃቅን ተቋማት አማካኝነት የስራ እድል እንደተፈጠረላቸው በተደጋጋሚ ሰምተናል። እውነታው ግን ከዚህ “ተአምራዊ ለውጥ” በእጅጉ ይለያል። ለተወሰነ ጊዜ የተወሰኑ ወጣቶች ስራ ያገኛሉ - ከመንግስት በኮንትራት እየተሰጣቸው። ኮንትራቱ ሲያልቅ፣ ስራቸው ሲቋረጥ ሌሎች ወጣቶች በሌላ ኮንትራት ለተወሰነ ጊዜ ስራ ይሰጣቸዋል። በጥቅሉ ሲደመር፤ ከሚሊዮን በላይ ሊሆን ይችላል። ስራ የተቋረጠባቸውን የምንቀንስ ከሆነ ግን፤ የወጣቶች የስራ አጥነት ችግር ብዙም ፈቅ እንዳላለ እንገነዘባለን። በእርግጥ፣ መንግስት ገና ከሆይሆይታ ስላልወጣ፤ ይህንን እውነት አሁኑኑ ለመቀበል ፈቃደኛ ላይሆን ይችላል። ውሎ አድሮ ግን፤ የስራ አጥነት ችግር አግጥጦ መታየቱ የማይቀር ነው። ውሎ አድሮ የአገሪቱ ኢኮኖሚ እየተቀዛቀዘ አይደል? ዡዋዡዌ ነው።

ፈር መያዣ:- “በታላቁ የሥነጽሑፍና የቋንቋ ሊቅ በዶ/ር ዮናስ አድማሱ ሕይወትና የኑሮ ልምድ ዙሪያ አንዳች ነገር የሚጽፍ እርሱ ማን ነው?” ብላችሁ ስትጠይቁት ተሰማው፡፡ እርሱም ቀድሞ ጠርጥሮ ነበር - ጋሽ ዮናስ ለዚህ ጽሑፍ ቅራቢ በድህረ ምረቃ መርሃ ግብር አስተማሪውና አማካሪው ነበር፡፡ በተለይ ይህ ፀሐፊ፣ የመመረቂያ ወረቀቱን ከ1951-1960 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በንጉሱ ፊት ሣይቀር ይቀርቡ በነበሩ “የኮሌጅ ቀን ግጥሞች” እና ገጣሚያን ማህበረ ፖለቲካዊ አመለካከትና ሂስ ላይ በማድረጉ ጋሽ ዮናስን የበለጠ ለማወቅ እድል አገኘ፡፡
ጋሽ ዮናስ የታላቅ ወንድሙን የዮሐንስ አድማሱን ፈለግ ተከትሎ፣ ከነሐይሉ ገብረዮሐንስ (ገሞራው)፣ ታምሩ ፈይሳ፣ አበበ ወርቄ፣ ኢብሣ ጉተማ ወዘተ. ጋር በውድድር ያሸነፈባቸውን ግጥሞች በኮሌጅ ቀን አቅርቧል፡፡ ዶ/ር ዮናስ እራሱም ተጠኝ የኮሌጅ ቀን ገጣሚ ስለነበረ የዚህን ጽሑፍ አቅራቢ ነፍስ ገዝቶ፣ በነፈስም በስጋም ተጣብቷል፤ ስለዚህ የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ፣ ስለሞጋቹ የሥነጽሑፍ ባለሟል ሕይወትና ክህሎት በወፍ በረርም ቢሆን ለመመስከር፣ ለአቅመ ፀሐፊነት ደርሷል፡፡
ለዛሬ በሕይወት ልምዱና ገጠመኞቹ ዙሪያ በጥቂቱ እናወጋለን፡፡ በአማርኛ ሥነጽሑፍ ንድፈ ሃሳብ አፍላቂነቱና በምርምር ሥራዎቹ ዙሪያ መረጃዎችን እያጣቀስን አካዳሚያዊ መጣጥፍ ለማስነበብ ደግሞ ለሣምንት ቀጠሮ እንይዛለን፡፡
ፀሐፊው፣ የእስከዛሬ አንቱታውን ትቶ፣ “አንተ” እያለ የተረከው፣ የመገናኛ ብዙሐን ቀልብ የሚስበው የዶ/ር ዮናስ የኪነጥበብ ሰውነት ሙያው ከሚፈቅደው የአነጋገር ዘልማድ ጋር እንደሰመረ እንዲፀና በሚል የተደረገ ትጋት እንጂ፣ አጉል ድፍረት እንዳልሆነ በትሁትነት ይገልፃል…
ከረሜላ፣ ቸኮሌትና ማስቲካ ይዞልን የሚመጣ መምህራችን…
በወርሃ ጥር፣ 2000 ዓ.ም ጋሽ ዮናስ የግማሽ መንፈቀ ዓመቱን ኮርስ ማጠቃለያ ሲያስተምር እጅግ ተመስጦ ነበር፡፡ “ለማስተማር ብቻ ተብለው የሚፈጠሩ የተለዩ ሰዎች አሉ፤ ሁሉም መምህር መሆን አይችልም!” የሚለውን የሥነ ትምህርት ፈላስፎችን አባባል ለማመን ከፈለጉ፣ ዶ/ር ዮናስ ሲያስተምር መመልከት ነበረብዎት… የውጭና የሀገር በቀል ንድፈ ሃሳቦችን እያረቀቀ፣ የአማርኛ ሥነጽሑፍን ሲያስተነትንና ሲፈክር ተማሪዎቹ አፋችንን እንደከፈትን እንቀራለን… በአካዳሚክ እውቀቱና በሕይወት ልምድ እውነቱ የሚያረቃቸው የሥነጽሑፍና የቋንቋ ሀቲቶች (ዲስኩርስ) እንደ ባህርማዶ ለስላሳ ሙዚቃ በተመስጦ ነው የምናዳምጣቸው፡፡ የሀቲቶቹን እና/ወይም የንድፈ ሃሳቦቹ ረቂቅነትን የምንመረምረው፣ የተመስጦ ሰበካውን ገታ አድርጐ እነዛኑ ሀቲቶች ገልብጦ “በፈርሱ” የጠየቀን ጊዜ ነበር…
ጋሽ ዮናስ ለማድነቅም ንፉግ አይደለም፡፡ ከተመስጦው መለስ ብሎ የሚጠይቀውን ውስብስብና አመራማሪ ጥያቄ የመለሰን ተማሪ፣ እስከ ጥግ ነው በአድናቆት የሚያመሰግነው፡፡

ያን ጊዜም አንድ ተማሪ የጋሼን ውስብስብ ጥያቄ መልሶ፣ ወሰብሰብ ያለ ሌላ ጥያቄ ጋሼን ሲጠይቀው …ጋሼ በሀሴት ፊቱ በራ… ወዲያው “…በዚህ ኮርስ A (ኤ) ሰጥቼሃለሁ… በዚህ ክፍለ ጊዜ አለመምጣት ትችላለህ! በቃ! ” አለው፡፡ የጋሽ ዮናስን ውስብስብ ጥያቄ መልሶ አድናቆት ማግኘት ትልቅ ክብር ስለሆነ፣ ሁላችንም በመላሹ ተማሪ ቀንተናል፡፡
በዚህ ጊዜ ታዲያ፣ ጋሽ ዮናስ ከኪሱ የተለያዩ ከረሜላዎችን አውጥቶ ለእያንዳንዳችን የድህረ ምረቃ ተማሪዎቹ በፍቅር ሰጠን፤ ወዲያው፣ በደስታና በአክብሮት ከረሜላችንን መብላት ጀመርን፤ ምክንያቱም፣ የያን ጊዜው የ65 ዓመቱ ጋሽ ዮናስ እሱም ከኛ ጋር ከረሜላውን ወደ አፉ ብሎ ነበርና፡፡ በነገራችን ላይ ዶ/ር ዮናስ ተማሪዎቹን ለመፈተን ሲጠራ፣ ቀድሞ በመፈተኛ ክፍሉ የእያንዳንዳችንን የፈተና ወረቀት በየመቀመጫችን አስቀምጦልን ይቆያል፡፡ ከፈተና ወረቀቶቹ ላይ ታዲያ ከረሜላ፣ ማስቲካና ቸኮሌት አይጠፉም…
በ”አማርዝኛ” የሚሳለቀው የቋንቋዎች ሊቅ
ዶ/ር ዮናስ፣ ተማሪዎቹ ይሁኑ የሥራ ባልደረቦቹ፣ በእውቀትም ይሁን በድንገት አማርኛና እንግሊዝኛ እየቀላቀሉ ጉራማይሌ ሲያወሩ ከሰማ፣ እንደሁኔታው ለዘብ አድርጐ በስላቅ ሊተቻቸው ይችላል፤ “ኧረ ይኼ አማርዝኛ አልገባኝም” በማለት፡፡ ወይም በቁጣ ሊወርፋቸው ይችላል፤ ‹‹አንጀባ አታብዙ!... ይኼ አማርዝኛችሁ አገር አጠፋ›› በማለት፡፡ “አማርዝኛ” ጋሽ ዮናስ፣ ለአማርኛና ለእንግሊዝኛ ድብልቅ የቋንቋ አጠቃቀም የሰጠው ስያሜ ይመስላል… ጋሼ ዮናስ የግዕዝ፣ የአማርኛና የእንግሊዝኛ ቃላት ስንጽፍ ወይም ስናነብ ከተደናቀፍን የቃሉን ስርወቃል (ወይም ግንድ) ከምንጩ እየቀዳ በየትኛውም ጊዜና ቦታ ሳይታክት ያርመናል… በቋንቋዎቹ ካለው ጥልቅ እውቀቱ የበለጠ፣ እኛ ተማሪዎቹን ለማረም ያለው ቀናነቱ በብዙዎቻችን አዕምሮ ገዝፎ ይታያል…
አስገራሚው የዶ/ር ዮናስ ቢሮ
የጋሽ ዮናስ ቢሮ፣ በስድስት ኪሎ ግቢ በማህበራዊ ሳይንስ ህንፃ ውስጥ፣ ከባህር ጠለል በላይ ሦስተኛ ፎቅ ጋ ይገኛል፡፡ በበርካታ መጻሕፍት የተጨናነቀው ይህ ቢሮ፣ ከበሩ ፊት ለፊት ሲቆሙ በስተቀኝ፣ ታዋቂው የሥነጽሑፍና ፎክሎር መምህርና ተመራማሪ የዶ/ር ፈቃደ አዘዘ ቢሮ ያዋስነዋል፡፡ በፊት ለፊት የታዋቂው የሥነልሣን ሊቅ የፕሮፌሰር ባየ ይማምና ባልደረቦቻቸው ቢሮዎች ያዋስኑታል… “ያለ ቀጠሮ ወደ ጋሼ ቢሮ መዝለቅ ፈጽሞ የተከለከለ ነው” ባይባልም፣ እንዲሁ ዘው ማለት የሚያስከፍለው ነገር ይኖራል፡፡ ዶ/ር ዮናስ በተለይ አጣዳፊ ሥራ ይዞ፣ ኮምፒውተሩ ላይ ተጥዶ ካገኙት ዝም ብሎዎት ሥራውን ሊሠራ ይችላል፤ በተለይ ያለ ቀጠሮ ከሆነ የመጡት፡፡ በሩን ደጋግመው እየቆረቆሩ ሰላም ከነሱት “የለሁም!” በማለት በመጀመሪያ በለሆሳስ ሊመልስ ይችላል፡፡ ደግመው ከቆረቆሩ ብስጭት ብሎ በመነሳት “የለሁም ስል አትሰማም!” በማለት ሊቆጣ ይችላል፡፡ ድንግጥ ብለው ከቆሙ፣ አያስችለውም ወዲያው መለስ ይልና፣ “ምን ፈልገህ ነው?“ ይላል… የጋሼን ጸባይ ያለመደ ተማሪ እንኳን ቢሮው ድረስ ሄዶ ቀርቶ፣ በመንገድ ሲያገኘው ሁሉ ይሸሻል፣ ይርበተበታል … ጋሽ ዮናስ ግን ይሄን አይነት መሸማቀቅ አይፈልገውም፤ ባህሪውን ያወቀ ተማሪ ግን የምሩን ተናዶ ቢቆጣ እንኳ፣ ሳይፈራ የደቂቃዎችን ክፍልፋይ ዝም ብሎ ካሳለፈው ወዲያው ምልስ ይላል… ጋሼ ሆዱ ገርና ቅን እንደሆነ፣ በአፉ ቢቆጣ እንኳን በሆዱ እንደማይቆርጥ ታዲያ፣ ከተወሰነ የጊዜ ቆይታ በኋላ ሁሉም ተማሪዎቹ ያውቃሉ፤ ያውቁታልም…
ጋሽ ዮናስ ሲቀልድ፣ በዘመንኛ ቋንቋ “ሲፎግር”፣ ሲጫወት… ይችልበታል፤ ተማሪዎቹ የማታለል ሙከራ ካደረግን፣ “እሣት የላስኩ የሱማሌ ተራ ጩልሌ ነኝ… ” በማለት ስቆብንና ተሳልቆብን ያልፋል…
አንድ ቀን የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ ተመካሪው እያለ፣ ደውሎ ለመምጣት ቀጠሮ ይቀበላል፡፡ በበነጋው ጋሽ ዮናስ ወደ ቢሮው ሲገባ ጠብቆ በቀጠሮው መሠረት ወደ እዚያው ያቀናል፡፡ ቢሮው ገርበብ ብሎ ሲያገኘው ከፈት አድርጐ ይገባና ይቆማል፡፡
ጋሽ ዮናስ “ምን ልታደርግ መጣህ?” አለው በቁጣ፡፡ ቀጠሮ እንዳለው ተናግሮ ተዝናንቶ ሲቆም፣ ጋሼ፣ “እኔ በእናንተ ማበድ አለብኝ… ደውለህ ነው መምጣት አላልኩህም!” በማለት ብስጭት ብሎ የሚማታበት “አለንጋ” ከጠረጴዛው ሲፈለግ፣ ተመካሪ የድህረምረቃ ተማሪው ፍንጥር ብሎ ከቢሮው ወጣ፡፡
የጋሽ ዮናስን ጸባይ ስለሚያውቅ ብዙ አልተደናገጠም፡፡ አንድ ሁለት እርምጃ ተራምዶ ሞባይሉን አወጣና ደወለ… ጋሼ ከቢሮው ውስጥ ሲስቅ ይሰማዋል፡፡ ወዲያው ስልኩ ተነሳ፤ “ምን ፈለግህ?” የሚል የለሆሳስ ድምጽ ተሰማ… “አይ ዛሬ ቀጠሮ ነበረኝ፤ ደውዬ እንዳስታውስ ተነግሮኛል!” ከማለቴ የጋሼ ሣቅ፣ ከሞባይሌም ከቢሮውም ተሰማኝ፡፡ እየሳቀ፣ “ና! አሁን ” አለኝ፡፡
ስህተቴ ሲገባኝ፣ ከቢሮው ሣልርቅ ወዲያው ደውዬ መጠየቄ ገርሞታል… በመልካም ፈገግታ ለ40 ደቂቃ ስመከር ቆየሁ… ወደ ዶ/ር ዮናስ ቢሮ ለመጀመሪያ ጊዜ ከሆነ የሚገቡት ብዙ የሚገርምዎት ነገር ሊያጋጥምዎት ይችላሉ… ጠረጴዛው በካኪ ፖስታ ታሽገው የሚታረሙ ወይም የታረሙ ወረቀቶች ተቆልለው ያያሉ - በአንድ ጠርዝ ላይ፡፡ የተለያዩ የታሸጉ ምግቦች፣ በጠርሙስ የተሞሉ የተለያዩ የከረሜላ፣ የቸኮሌት አይነቶች ይመለከታሉ፡፡
በጠረጴዛው ሌላኛው ጫፍ፣ ሽንኩርት፣ እንቁላል፣ በላስቲክ የታሸጉ የተለያዩ ቅመማ ቅመሞች ሊያዩ ይችላሉ፡፡
በጠረጴዛው መካከል ላይ የተለያዩ መፃሕፍት ለንባብ ተሰድረዋል … ገሚሶቹ መፃሕፍት ተገልጠው ተገልጠው በአፋቸው ተደፍተው ያያሉ… በጠረጴዛው በውስጥ በኩልም (በግርጌው) የተለያዩ መዝገበ ቃላት፣ የጥናት መጽሄቶች /ጆርናሎች/… መቆለላቸውን የሚያዩት፣ አንድ መጽሐፍ ገልጦ ከእንግዳ መቀበያ ወንበር ተነስተው ወደ እርሱ ጠረጴዛ ቀርበው ካነበቡ ወይም የተሰወረበትን መፃሕፍት እንዲያፋልጉት ከፈቀደ ነው፡፡
ከጠረጴዛው ጀርባ ታዲያ፣ ከምሣ በኋላ የሚያርፉበት ይመስለኛል ባለ ሦስት ቀጫጭን ስፖንጅ ተጣጣፊ ፍራሽ፣ በስርአት ተጣጥፎ የጠረጴዛውን እግር ተደግፎ ሊያዩ ይችላሉ፡፡
ትንሽ የኤሌክትሪክ ምድጃ፣ ተቀምጧል፡፡ የአንድ የመካከለኛ ሰው እጅ መዳፍ የሚጨብጠው ዓለት የሚመስል ድንጋይ ጠረጴዛው ስር ወይም ላይ ቁጭ ብለው ቢያዩ አይደንግጡ… ጋሼ ተማሪዎቹ ቶሎ ከቢሮው አንወጣለት ስንል ድንጋዩን እያሳየ ያስፈራራናል - እየቀለደና እየሳቀ ነው፡፡ ተማሪዎቹም ጋሽ ዮሐንስ ለየት ያለና ዘመናዊ ሰው እንደሆነ እናውቃለን… በነገራችን ላይ የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ የጠረጴዛውን ጀርባ ለመጨረሻ ጊዜ ያየው በሀምሌ ወር 2002 ዓ.ም ነበር፡፡
የህልፈተ ህይወት ጊዜውን የተነበየበት አጋጣሚ
በጥር ወር 2004 ዓ.ም በዋቢሸበሌ ሆቴል፣ የበድሉ ዋቅጂራን (ዶ/ር) ሁለተኛ የግጥም መጽሐፍ /“እውነት ማለት የኔ ልጅ”ን/ ለማስመረቅ “ዛጐል ቤተመፃሕፍት” ዝግጅቱን አጠናቋል፡፡ ዶ/ር በድሉ የግጥም ስብስቡ “መታሰቢያነቱ ሀውልት ላልቆመላቸው ለዮሐንስ አድማሱ እና ለደበበ ሰይፉ” እንዲሆንለት በማድረጉ፣ ዶ/ር ዮናስ በዚህ ዕለት በመድረክ ላይ ንግግር እንደሚያደርግ ይጠበቃል፡፡ የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ፣ ወደ መድረኩ ሲመለከት፣ የመጽሐፍ ምረቃ በሚያበስረው “ባነር” ላይ አንድ ቃል ያያል፤ የዛጐል ቤተመፃሕፍት ሥራ አስኪያጅ የሆነውን እንዳለጌታ ከበደን ጠርቶ፣ “ዶ/ር ዮናስ ያን ካየ መናገሩ አይቀርም - መላ ፈልግ” ይለዋል፡፡
ጋሽ ዮናስ ወደ መድረክ ሲጋበዝ፣ “… ይኸው! የግጥም ‹መድብል› አይባልም፤ መድበል እንጂ!” በማለት የቃሉን ሥርዎ አመጣጥ በማብራራት ንግግሩን ጀመረ፡፡ ስለ ዮሐንስ አድማሱ ሕይወትና ሥራዎች አብራራ… በተለይ ዮሐንስ በባለቅኔውና ፀሐፌ ተውኔቱ ዮፍታሔ ንጉሴ ሕይወትና ሥራዎች ዙሪያ የሠራውን የምርምር ሥራ “በአሰናኝነት” አሰናድቶ እያጠናቀቀ መሆኑን ተናገረ፡፡ በመጨረሻ፣ “…ይኼ መጽሐፍ ታትሞ ሳላየው እግዚአብሔር እንዳይገለኝ!” በማለት “ፈጣሪውን” በሰከነ መንፈስ የተማፀነበት አጋጣሚ በቦታው የነበረን ሰው ሁሉ አሳዝኗል፡፡
ጋሽ ዮናስ፣ የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበረ ባሳተመው “የዘመን ቀለማት” የግጥም መድበል ላይ፣ “ህዳር 6 ቀን 1935 ዓ.ም ቅዳሜ ሌሊት በዐሥር ሰዓት በአዲስ አባ ከተማ በደጃች ውቤ ሠፈር” መወለዱን እራሱ በከተበው የሕይወት ታሪኩ ተናግሯል፡፡ ከመጽሐፍ ቅዱሱ ገድለኛ፣ ከነቢዩ ዮናስ ስሙን ብቻ ሳይሆን ግብሩንም የወረሰ የሚመስለው ዶ/ር ዮናስ አድማሱ፣ ህልፈቱ እስከታወቀበት የካቲት 1 ቀን 2005 ዓ.ም ድረስ፣ የዶክትሬት ዲግሪ ተማሪዎቹን እያማከረ፣ እያነበበ፣ እየፃፈ ያለፈ ታላቅ ምሁር መሆኑ በተግባር አሳየ፤ እስከመጨረሻዋ የሕይወት ጠብታ መፃሕፍት ታቅፎ ለዘላለሙ ያንቀላፋ የቀለም ቀንድ!
እውቀት የሚቀምርባት አስገራሚ ቢሮውም ወዳጇ ጋሽ ዮናስ ለዘላለሙ ከተለያት በኋላ ሁሉ፣ የሥነጽሑፍ ሊቀሊቃውንቷ ህልፈት በስድስት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ እስከታወጀበት የደቂቃዎች ክፍልፋይ ድረስ፣ ይህቺ የቀለም መጥመቂያ ቢሮው፣ በበር ሥር የተላከላትን የተመካሪ ተማሪዎች የምርምር ፕሮፖዛል በአደራነት ስትቀበል ነበር… የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ የዶ/ር ዮናስን እርፈት ከቀኑ 8 ሰዓት አካባቢ ከመስማቱ በፊት፣ የጋሽ ዮናስ የዶክትሬት ዲግሪ ተመካሪ ተመሪው የፕሮፖዛል ወረቀቷን ወደ 5 ሰዓት አካባቢ በበር ስር ማስገባቱን ሰምቷል…
የተስፋዋን ቀን ለማየት 12 ቀን ሲቀራት የተነጠቀች ነፍስ
ታዋቂው ባለቅኔና ለውጥ አራማጁ መምህር ዮሐንስ አድማሱ በ1967 ዓ.ም በድንገት በ37 ዓመቱ ሲቀሰፍ፣ በዮፍታሔ ሕይወትና ክህሎት ዙሪያ እያገባደደው የነበረውን የምርምር ሥራ አጠናቆ ማሳተም፣ በታናሽ ወንድሙ በጋሽ ዮናስ አድማሱ ትከሻ ላይ አረፈ፡፡
ከ35 ዓመት በላይ ሳይታተም የቆየውን የምርምር መጽሐፍ የህትመት ብርሃን እንዲያይ፣ እነ ፕሮፌሰር ማስረሻ ፈጠነ፣ ዶ/ር ዮናስን ሲያበረታቱ ቆይተዋል…
የተለያዩ ሃገራዊ ጉዳዮችን የሚያወሱ ዘመን ተሻጋሪ መጻሕፍት፣ ከተቀበሩበት ጉድጓድ እየወጡ፣ ከሻገቱበት ቦታ እየተራገፉ እንዲታተሙ ያደረጉትና ለዘላቂ የህትመት ሥራ መሠረት የጣሉት እነ ፕሮፌሰር ማስረሻ እና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ፕሬስ የቦርድ አባላት፣ ፕሮፌሰር ማስረሻ፣ በዶ/ር ዮናስ አሰኛኘት ለህትመት የበቃውን መጽሐፍ፣ በልዩ ሁኔታ ለማስመረቅ ከሌሎች ባልደረቦቻቸው ጋር የቁርጥ ቀን ቀጠሮ ይዘዋል… የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ አርታኢና የጋዜጣ አምደኛው ብርሃኑ ደቦጭ የካቲት 13 ቀን 2005 ዓ.ም “በብሔራዊ ትያትር” አዳራሽ የዮሐንስን መጽሐፍ ለማስመረቅ ደፋ ቀና እያለ፣ ከዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ ጋር ተገናኙ፡፡
ጋሽ ዮናስ የመጽሐፉን ህትመት ሳላይ እንዳልሞት በማለት በጉጉት የሚጠብቃትን ዕለት፣ የሦስት ታላላቅ የሥነጽሑፍ ባለሟሎች ጠንካራ የኪነት ክንድ ያረፈበት መጽሐፍ የሚመረቅባትን ያቺን ቀን እኔም በጉጉት እየጠበቅሁ ነው፤ በዚች ታሪካዊ ዕለት፣ ዮሐንስ አድማሱን የሚዘክር አንድ የሥነ ጽሑፍ ሥራ ለማቅረብ እየተሰናዳሁ ነበርና፡፡
የዶ/ር ዮናስ አድማሱ ነፍስም ከ35 ዓመት በላይ ታግሣ የጓጓችለትን የተስፋ ቀን ለማየት 12 ቀናት ብቻ ቀርተዋት እያለ፣ እኔም ወጉ ደርሶኝ ከመምህሬ ከጋሽ ዮናስ ፊት፣ አብዮተኛው የኮሌጅ ቀን ገጣሚ ዮሐንስ አድማሱን ለማውሳት 12 ቀናትን እየተጠባበቅሁ እያለ፣ የታላቁ የቀለም ቀንድ የጋሽ ዮናስን ህልፈተ ሕይወት በድንገት መስማት ምን ያህል ያስደነግጥ!?

 


ባንተ በኩል ፈካች
ነ.መ
የልቤን ማኅደር፣ ቆፍሬ ቆፍሬ፤
ያገር ውለታህን ልናገር አምርሬ፡፡
ምንም ቢደባለቅ፣ ብስሉ ከጥሬ
የፊደል ልሣኑ፣ ያው ይጫሃል ዛሬ፡፡
ምን ቢበረክቱ፣ የእኛ ነው የሚሉ
አገሩና ህዝቡ፣ ድሉም ሆነ ትግሉ
ቢከትቡ፣ ቢያውጁ፣ ገድል ቢያሳቅሉ
በደም የተፃፈ፣ ይጎላል ከሁሉ!!...(“ጐ” እና “ላ” ይላላል)
ለመሰነባበት፣ ጊዜው አልነበረን…(“መ” እና “ሰ” ይጠብቃል)
መቼስ ያቃል ኖሮን፡፡
ለመሰነባበት ጊዜም አልነበረህ…(“መ” እና “ሰ” ይላላል)
መቼስ ያቃል ኖሮህ!!
ብቻህን ሄደሃል፣ ያው ብቻህን ኖረህ፡፡
እንደ ጊዜው ባህል፣ ጥንት እኔ እንደማቅህ
ከመሬቱ በታች፣ ከዕውነት ጋር ተቀብረህ
መብራት የማያቆም፣ የንቁ ኮከብ ነበርክ፡፡
ጥንት ገና ዱሮ፣ ሰው የነበርን ቀን
ጭቆና ሲመረን፣ ግፍ ሲያንገፈግፈን
ልብ ለልብ ማውራት፣ እንዲህ ሳይቸግረን፤
የብዕሬን ዕንባ
ለአገሬ ሳነባ፤
ብታይልኝ ብዬ -
“አበባ” እሚል፣ ግጥም ልኬልህ ነበረ፡፡
እንዲህ መለስክልኝ
መቼም አይረሳኝ:-
“በጧት ቸግነሃል፣
በጧት ጀግነሃል፣
የለብህም ዕዳ፤
አበባህ ግጥም ናት፣ ሁልጊዜ ትፈንዳ!”
ይኸው ላንተም ተርፋ፣ ባንተ በኩል ፈካች
ታሪክ ያለው ትውልድ፣ መኖሩን አወጀች!!
(ለዮናስ አድማሱና ለትውልዳችን)
የካቲት 8/2005