Administrator

Administrator

ከአብርሽ ጋር ሲያዩኝ “ኮንግራ ሙሽራው ተገኘ?” ይሉኛል…

ፈረንሳይ ትንሿ የኢትዮጵያ ሆሊዉድ ትባላለች…

የጠበሰም የተጠበሰም፤ የጠየቀም የተጠየቀም የለም (ስለትዳሯ)

በአዲስ አበባ ውስጥ ፈረንሳይ ለጋሲዮን ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ተወልዳ አድጋለች፡፡ ከልጅነቷ ጀምሮ ማንጐራጐር ይቀናት የነበረችው ትንሿ አበባ፤ እንጉርጉሮዋን በማሣደግ በቀበሌ ክበብ አድርጋ፣ በምሽት ክበብ አቋርጣ እስከ ትልቁ ብሄራዊ ቴአትር ቤት ጉዞዋን ቀጥላለች፡፡ ከድምፃዊነት በተጨማሪ በቴአትር መድረክም ላይ ችሎታዋን ያሣየችበትን “ልደት” ቴአትርና “አንድ ምሽት”ን ሠርታለች፡፡ ወደ ፊልሙም ሠፈር ጐራ ብላ “ሩሀማ” እና “ሠካራሙ ፖስታ” ላይ ተውናለች፡፡ ማስታወቂያውንም ሞክራለች፡፡ “ሙሽራዬ ቀረ” የሚል ተወዳጅ አልበም አውጥታ በጣም ተወዶላት ነበር፡፡ አርቲስቷ አምስት ዓመት ገደማ ድምጿን አጥፍታ ከቆየች በኋላ ሠሞኑን “የለሁበትም” የተሠኘ አዲስ አልበም ለማውጣት ደፋ ቀናውን ተያይዛዋለች፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛዋ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ከአበባ ደሣለኝ ጋር በነበራት ቆይታ በአዲሱ ስራዋ፣ ጠፍታ ስለከረመችበት ጉዳይና ሌሎችንም የሥራና የህይወት ቁምነገሮች አንስታ ተጨዋውተዋል፡፡ እነሆ:-

የት ጠፍተሽ ከረምሽ?

ጠፋ ብያለሁ ግን ሥራ እየሠራሁ ስለነበር ነው፡፡ አሁን በአዲስ ስራ እየመጣሁ ነው፡፡ እስከዛሬ ቅጽል ሥም እንዳለሽ አልነገርሽንም? አንቺ ከየት ሰማሽ? እኔ ሰሞኑን ሰምቻለሁ፡፡ ከራስሽ እንስማው…

ማነው ቅጽል ስምሽ?

የሚገርመው ወደ ኪነ-ጥበብ ገብቼ ከ “እርጂኝ አብሮ አደጌ” እስካሁን ድረስ ብዙ ቃለ - ምልልስ አድርጌያለሁ፡፡ እኔም አልተናገርኩም፡፡ ሰዎችም ቅጽል ስም እንዳለኝ አያውቁም፡፡ ሰምቶም የጠየቀኝ የለም፤ አንቺ የመጀመሪያ ነሽ ስለ ቅጽል ስሜ ስትጠይቂኝ ማለቴ ነው፡፡ ስሜ “ሙናና” ነው የሚባለው፡፡ ይሄንን ስም ቤተሰቤ፣ እህቶቼ፣ የቅርብ ዘመድ እና የሠፈር ሰው ነው የሚያውቀው፡፡ ምን ማለት ነው? ስወለድ በጣም ቀጫጫና ትንሽ ነበርኩኝ አሉ፡፡ ካደግኩም በኋላ መወፈር አልቻልኩም፡፡ እና አሁን ይህቺ ሰው ሆና ታድጋለች… የሆነች ሙንን ያለች ነገር ብላ አያቴ ስትናገር፣ በዛው ሙናና ተባልኩኝ፡፡ አንዳንዶቹ ሙኒኒ ብለው ይጠሩኛል፤ ሰፈር ውስጥ ማለት ነው፡፡

እዚህ ለመድረስ ውጣውረዶችን እንዳሳለፍሽ ይነገራል፡፡ እስኪ አጫውቺኝ?

ከሌሎች ሰዎች በጣም የተለየ ውጣ ውረድ አይደለም ግን እንደማንኛውም ባለሙያ እዚህ ለመድረስ ከፍና ዝቅ ይኖራል፡፡ ምክንያቱም አንድ ነገር ሲጀመር ሁሉም አልጋ በአልጋ አይሆንም፤ በየትኛውም የስራ ዘርፍ ቢሆን ማለት ነው፡፡ ፈተናዎቹ እንግዲህ ከክበብ ጀምሮ እስከ ቴያትር ቤት፣ ከዚያም አልበም እስከማውጣት ደፋ ቀና ማለት ያለ ነው፡፡ ናይት ክለብ ስሰራም እንደዚሁ ሴትነትሽን ተከትለው ከሚመጡት ፈተናዎች ጀምሮ የተለያዩ ነገሮች አሉ፡፡ ዋናው ነገር እነሱን በድል ተወጥቼ እዚህ መድረሴ ነው፡፡ ይህ እንግዲህ እግዚአብሔርም ተጨምሮበት ነው፡፡ ከልጅነትሽ ጀምሮ ታንጐራጉሪ ነበር፡፡ በዛን ጊዜ የእነማንን ዘፈን ትዘፍኚ ነበር፡፡ የሂሩትን ዘፈኖች ለመጫወት የመረጥሽበትስ ምክንያት ምንድን ነው?

በነገርሽ ላይ ልጅ ሆኜ የወንድም የሴትም ዘፈን አይቀረኝም፡፡ ሁሉንም በቃ መዝፈን ነው፡፡ ለምሳሌ ደረጀ ደገፋውና ማርታ ሀይሉ እየተቀባበሉ የሚዘፍኑትን “አንቺ ሆዬ ሆይ” የተሰኘ ዘፈን፣ የሷንም የእሱንም ራሴን በራሴ እየተቀባበልኩ እዘፍን ነበር፡፡ ወንዱንም ሴቷንም እየሆንኩ ማለቴ ነው፡፡ የኬኔዲና የየሺመቤትን ዘፈን አሁንም ወንዱንም ሴቷንም ሆኜ እዘፍን ነበር፡፡ የጋሽ ጥላሁንንም እዘፍናለሁ፡፡ ያው ልጅ ስትሆኚ መምረጥ የለም፡፡ ሁሉንም መነካካት ነው፡፡ ከዚያ በኋላ መዝፈን ማለት ምን እንደሆነ፣ ሜጀር ማለት ምን ማለት እንደሆነ ሲገባሽ፣ መድረክ አያያዝ፣ ማይክ አጨባበጥ ምን እንደሆነ ስታውቂ፣ የማንን ዘፈን ብዘፍን ለድምፄ ከለር ይስማማል በሚል መምረጥ ትጀምሪያለሽ፡፡ እኔም ይሄ ሲገባኝ የፍቅር አዲስን፣ የብዙነሽ በቀለን፣ የሂሩትን፣ የማርታ ሀይሉን እና የሌሎችንም በመዝፈን ነው ወደራሴ የመጣሁት፡፡ የሂሩትን ዘፈን የዘፈንኩት የተለየ ምክንያት ኖሮኝ ሳይሆን ዘፈኖቹን በጣም ስለምወዳቸው ነው፡፡ ናይት ክለብ (የምሽት ክለብ) ውስጥ ረዘም ላለ ጊዜ እንደመስራትሽ ብዙ ገጠመኞችና ፈተናዎች ይኖሩሻል ብዬ አስባለሁ፡፡

እስኪ ከገጠመኞችሽ ጥቂት አውጊኝ? ናይት ክለብ ስሠራ የተለየ የገጠመኝ ነገር የለም፡፡

ግን አምሽቼ ስወጣ ቤቴ ሩቅ ስለነበር ለመሄድ እቸገር ነበር፡፡ የሚያደርሰኝ ሰርቪስ የለም፡፡ ፈረንሳይ ለጋሲዮን ድረስ መሄድ ለእኔ ትልቅ ፈተና ነበር፡፡ አንዳንዴ ጓደኛዬ ቤት ሳድር ቤተሰቤ ይጨነቃል፡፡ በግድ ነው እንጂ እንድሠራም አይፈቀድልኝም ነበር፡፡ ሌላው በወቅቱ ተማሪ ስለነበርኩኝ ደብተር ይዤ ናይት ክለብ የምሄድበት ጊዜ በርካታ ነበር፡፡ በተለይ ፈተና የደረሰ ሰሞን አንድ እዘፍንና እንደገና ደብተር ይዤ እቀመጣለሁ፡፡ በዚህ መልኩ ነው 12ኛ ክፍልን የጨረስኩት፡፡ ከዛ በተረፈ ናይት ክለብ ስትሠሪ የሚወድሽ ይኖራል ወይም የሚናደድብሽ ይኖራል፡፡ በርቺ አሪፍ ነው የሚልሽ ይኖራል፡፡ የሚያመናጭቅ ይኖራል፤ ይሄን ሁሉ አልፌያለሁ፤ የተለየ ገጠመኝ ግን የለኝም፡፡

ስለ ብሔራዊ ቴአትር ቤት ቆይታሽ እናውራ፡፡

ብሔራዊ ቴአትር ቤት ታሪካዊና ቀዳማዊ እንደመሆኑ እዛ በቋሚነት ለመቀጠር ብዙ እንደሚለፋ ሰምቻለሁ አንቺ እድሉን አግኝተሽ ለስምንት ወይም ለሰባት ዓመት ያህል ሰርተሽ እንደገና በራስሽ ፈቃድ መልቀቅሽን ነው የሰማሁት እንዴት ለቀቅሽ? እውነት ለመናገር ብሔራዊ ቴአትርን በጣም ነው የምወደው፡፡ ስገባም ፀልዬ ፈጣሪዬን ለምኜ እንደውም ተስዬ ብል ነው የሚቀለኝ፤ እንደዛ ነው የገባሁት፡፡ እንዳልሽው ብሔራዊ ቴአትር ቤት ትልቅ ቤት ነው፤ ብዙ ባለሙያዎችን ያፈራ ነው፤ አሁንም ብዙ ሙያተኞች አሉት፡፡ በዛን ሰዓት ከክበብ ተነስሽ በአንዴ ቴአትር ቤት መግባት ትልቅ ነገር ነው፡፡ ይሄ ከዛሬ ዘጠኝና አስር ዓመት በፊት ነው፡፡ እዛ በመስራቴ እና የታሪኬ አንድ አካል በመሆኑ ደስተኛ ነኝ፡፡ በወቅቱ 20 ሰው ተወዳደረ፤ የሚፈለገው ግን አንድ ሰው ነበር፡፡ ምንም እንኳ ማስታወቂያውን አይቼ መጀመሪያ ብመዘገብም የፈተናው ቀን ግን በጣም አረፈድኩኝ፡፡

በምን ምክንያት?

ባስ አጥቼ ሁሉም ሰው ተፈትኖ ካለቀ በኋላ ደረስኩኝ፡፡ ከዚያም ፈታኞቹን እባካችሁ ብዬ ለምኜ፣ እስኪ እንያት ተብሎ እድል ተሰጠኝ፤ ግን ፈጣሪ ተጨምሮበት ፈተናውን አልፌ ተቀጠርኩኝ ማለት ነው፡፡ በወቅቱ ስትቀጠሪ በድምፃዊነት ነበር፡፡ ከዚያ ቴአትርም ሰርተሻል፤ ኧረ ተወዛዋዥም ነበርሽ ነው የሚባለው፡፡ እውነት ነው?

ለመጀመሪያ ጊዜ የተጫወትሽውን ቴአትርም በዚያው ንገሪኝ …?

እርግጥ የተቀጠርኩት በድምፃዊነት ነው፡፡ ቴአትር ስሠራ አይተውኝም አያውቁም፡፡ ነገር ግን የቀበሌ ክበብ ውስጥ ቴአትር እሠራ ነበር፡፡ ሲራክ ታደሰ ያዘጋጀው “ልደት” የተሰኘ ትርጉም ቴአትር ነበር፡፡ በወቅቱ ካስት ሲያደርጉ “ይህቺ ልጅ ያቺን ገፀ ባህሪ ታመጣታለች” ብለው መረጡኝ፤ ስፈተንም አለፍኩኝ፤ እሱን ቴአትር ስጫወት ከእነ አርቲስት ጌታቸው ደባልቄ፣ ተስፋዬ ገ/ሀና፣ ትዕግስት ባዩ፣ ሱራፌል ወንድሙ ጋር ነበር፡፡ እነዚህ ትልልቅ አርቲስቶች ናቸው፡፡ በቴሌቪዥን አይቼ ከማደንቃቸው ጋር በአንዴ ተቀላቀልኩኝ፡፡ ቴአትሩ ለአንድ አመት ታይቷል፡፡ ከዛም በኋላ በደብል ካስት ልምምድ አደርግ ነበር፡፡ “ልደት” ቴአትር ላይ በጣም ተሳክቶልኛል፡፡ እንደነገርኩሽ በክበብ ደረጃ ድምጽም፣ ቴአትርም፣ ውዝዋዜም እሠራ ነበር፡፡ ውዝዋዜውን የተውኩት አጭር ስለሆንኩ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ “አንድ ምሽት” የሚል ቴአትር የጐዳና ሴተኛ አዳሪ ሆኜም ሰርቻለሁ፡፡ ትንሽ ክፍል ብትሆንም ስጫወት ጥሩ ነበርኩኝ፡፡ እንዲህ እንዲህ እያልኩ ነው የቆየሁት፡፡

ታዲያ እንዴት ቴአትር ቤቱን ለቀቅሽ?

እንደምታውቂው የሰው ልጅ አንድ ቦታ ላይ አይቆምም፡፡ ፍላጐት እየጨመረ ሲሄድ ነገ የተሻለ ነገር ማግኘት ይፈልጋል፡፡ እኔም የማደግ የመለወጥ ተስፋ ነበረኝ፡፡ እዚያው ቴአትር ቤት እያለሁ “እርጂኝ አብሮ አደጌ” የተሰኘው ከትዕግስት ፋንታሁን ጋር የሠራሁት አልበም ወጣ፡፡ ከዚያ በኋላ ለስራ ወደ ውጭ እፈለግ ጀመር፡፡ ፈቃድ ወስጄ ወጣ ብዬ ሠርቼ እመለስ ነበር፡፡ በመሀል ነጠላ ዜማም መስራት ጀመርኩኝ፡፡ በመጨረሻ “ሙሽራዬ ቀረ” አልበሜ ወጣ፡፡ በዚህ ጊዜ ከበፊቱ የበለጠ የውጭ ጥሪዎች መብዛት ጀመሩ፡፡ አንዴ አረብ አገር፣ አንዴ አውሮፓ ማለት ጀመርኩኝ፡፡ በመጨረሻ ግን አሜሪካ የተጠራሁበት ሥራ የስድስት ወር ስለነበር ፈቃድ አልሰጡኝም፡፡ እንደነገርኩሽ መለወጥ ማደግ ስለምፈልግ፣ ለስድስት ወር የምትሄጂ ከሆነ ትለቂያለሽ የሚል ነገር መጣ፤ እሺ ብዬ ሄድኩኝ ማስታወቂያ ተለጠፈብኝ፤ በዚህ ምክንያት ነው ቴአትር ቤቱን የለቀቅኩት፡፡ እንደሰማሁት ሰሞኑን ያንቺን ህይወት የሚዳስስ፣ ግለ ታሪክሽን የሚናገር ዘጋቢ ፊልም (ቪዲዮ) እያሠራሽ ነው፡፡ ስለሱ ጉዳይ ትንሽ ብታብራሪልኝ?

እዚህ አገር የተለመደው አንድ ሰው ሲሞት ታሪኩ ከዚህም ከዚያም ተለቃቅሞ ለአንድ ጊዜ ብቻ እከሌ በዚህ ጊዜ ይህን ሰራች (ሠራ)፣ የህይወት ዘመኑ ይህን ይመስላል ተብሎ በዚያው ይረሳል፡፡ ይሄ ከሚሆን አንድ ሰው በህይወት እያለ ትክክለኛ ግለ ታሪኩ የት ተወልዶ የት አደገ፣ የት ተማረ፣ በህፃንነቱ ምን አይነት ሰው ነበር፣ መልኩስ አስቀያሚ ነበር፣ ባህሪውስ? የሚለውን ኦውቶባዮግራፊ ቢያሰራ ጥሩ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ በአንድ በኩል ደግሞ ፕሮሞሽንም ነው፡፡ ምናልባት አበባን ሰው የሚያውቃት “እርጂኝ አብሮ አደጌ”ን ከሠራች በኋላ ሊሆን ይችላል፤ ከዚያ በፊት የነበራትን ነገር አያውቀውም፤ ምን አይነት ፈተናዎችን አልፋለች፣ አይናፋር ነበረች ወይስ በልጅነቷ ረባሽ ነበረች፣ በትምህርቷስ ውጤቷ ምን ይመስል ነበር፣ የሚሉትንና መሰል ጉዳዮችን ሰው ቢያውቀውና ከአሁኑ ማንነት ጋር ቢያስተያየው ደስ ይላል በሚል ቪዲዮውን እያሰራሁ ነው፡፡ አንቺ አሁን ገና ከወጣትነቱ አልወጣሽም፤ ከአንቺ ብዙ ስራዎች ይጠበቃሉ፤ የግለ ታሪኩ ስራ ትንሽ አልፈጠነም?

እንዳልሽው ብዙ ይጠበቃል፤ ያኔ አሁን በተሰራው ላይ እየተጨመረ ስለሚሄድ አሁንም ቢሠራ ችግር አለው ብዬ አላስብም፡፡ አሁን መሠራቱ እንደውም ወደፊት በእኔ መንገድ መጓዝ ለሚፈልግ ብዙ ትምህርት ይሆነዋል፡፡ በአንድ ነጠላ ዜማ ተነስቶ ታዋቂ መሆን እንደማይቻል፣ ብዙ ውጣ ውረድ እንዳለ፣ እንዴት መታለፍ እንደሚችል ይማሩባታል ብዬ አስባለሁ፡፡ በተረፈ ቅድም እንዳልኩሽ በልጅነቴ ያለው ነገሬ የሚያስቅም ነገር ይኖረዋል እና የሚያዝናና ይሆናል፡፡ ለምሣሌ የዱሮ ፎቶዬን ሲያዩ “እንዴ አባባ እንደዚህ አስቀያሚ ነበረች?” አሊያም “ወይኔ ስታምር” የሚሉ ይኖራሉ እና ሊያዝናና ይችላል ብዬ አስባለሁ፡፡

“እርጂኝ አብሮ አደጌ”ን ከዘመድሽ ከትዕግስት ፋንታሁን ጋር ሠርታችሁ ተወዶላችኋል፤ ከዚያ በኋላ አብራችሁ አላየናችሁም፡፡ ለምን ቆመ?

የሚገርምሽ የቆመ ነገር የለም፡፡ በእኔና በቲጂ መካከል ያለው ግንኙነት የቆመ ይመስላል እንጂ አልቆመም፡፡ እንሠራለን፣ በየቀኑ እንገናኛለን፣ በየጊዜው እንደዋወላለን፡፡ ነገር ግን የህይወት መንገድ አንዳንዴ አስቸጋሪ ነው፡፡ በተለይ ባለ ትዳር ስትሆኚ፣ ልጅ ስትወልጂና የቤተሠብ ሀላፊ ስትሆኚ ቤቴን ቤቴን ይመጣል፣ ወይ እኔ ተነስቼ ለስራ አንዱ አገር እሄዳለሁ፣ ቲጂም ተነስታ ወይ አሜሪካ ትሄዳለች፡፡ አየሽው አሁን የህይወት ጐዳና ወዲያና ወዲህ እንደሆነ፡፡ በዚህ ምክንያት እንደድሮው ተረጋግቶና ተጣምሮ ለመስራት ይከብዳል፡፡ ሩጫው አልገጣጠም ብሎን ነው ያልሠራነው፤ በሌላው ግንኙነታችን አብረን ነን፡፡ አሜሪካም በአንድ ወቅት አብረን ሠርተናል፡፡ ለምሣሌ የዛሬ ሁለት ዓመት አሜሪካ አንድ ቤት ነበርን፤ አብረን ሠርተናል፤ ቱር አብረን ነበር የምንወጣው እና ይሄን ይመስላል፡፡ “ሙሽራዬ ቀረ” የተሠኘውን ዘፈን ስትጫዎቺ ሙሽራዉ የእውነት የቀረ ያህል ስሜትን ጨምድዶ ይይዛል፡፡ ለዘፈን ብለሽ ሳይሆን የደረሠብሽ ነው የሚመስለው፡፡ ሙሽራ የቀረበት ዘመድ ወዳጅ አጋጥሞሻል ወይስ በቅርብ የምታውቂው ጉዳይ አለ?

የህዝቡስ ምላሽ ምን ይመስላል?

የሚገርምሽ ነገር “ሙሽራዬ ቀረ” በጣም ተፅዕኖ የፈጠረ ስራ ነው፡፡ አሁንም ድረስ ወይ ከአብርሽ ጋር (ባለቤቷ ነው) ሲያዩኝ ወይም የጋብቻ ቀለበቴን ሲያዩት “ኮንግራ ሙሽራው ተገኘ?” ይሉኛል፡፡ በእኔ ላይ ደርሶ የዘፈንኩት የሚመስላቸው አሉ፡፡ በአጋጣሚ ሀሣቡ መጣ፣ አብርሽ ፃፈው፤ ሮማን አየለ ዳይሬክት ስታደርገው የባሠ ነፍስ ዘራና እንዲህ አነጋጋሪ ዘፈን ሆነ፡፡ በጣም ተመስጬ የእውነት አስመስዬ የሠራሁት ቁጭ ብዬ ስሜቱን አስበው ስለነበር ነው፡፡ ይሄ ዘፈን በወጣ ሠሞን ብዙ ሙሽሮች ቀርተው፣ ድግስ አበላሽተው በ“ፖሊስና ህብረተሠብ” ፕሮግራም ላይ መመልከት ጀምረን ነበር እኮ፡፡ አጋጥሞሻል?

አጋጥሞኛል፤ አይቻለሁ፡፡ እኛ ባንሠማና ባናይ በየቦታው ይሄ ነገር ይከሠታል፡፡ እስኪ አስቢው የእኛን አገር ባህል? አንድ ሴት ተዘጋጅታ ድግስ ተደግሶ፣ ወዳጅ ዘመድ ተሠብስቦ፣ ሙሽራው ሲቀር ምን ያህል እንደሚያሸማቅቅ፡፡ በዘፈኑ እኔ መንገድ ስከፍት፣ ብዙ ሠው ሙሽራው እንደቀረ በክስ መልክ መናገርና ፖሊስም ለማስተማር በቴሌቪዥን ሲያሣየን ነበር፤ ብቻ ዘፈኑ የማንንም ቤት ሊያንኳኳ የሚችል፣ ያንኳኳባቸውንም ብሶት የቀሠቀሠ ስለሆነ በጣም ተወዶ ተደምጧል፡፡

ከሙዚቃና ቴአትር ባሻገር በ “ሩሃማ” እና “ሠካራሙ ፖስታ” ላይ በፊልም ትወና ብቅ ብለሽ ነበር፤ አሁን እልም ብለሻል፡፡ ማስታወቂያም ላይ ተመልክተንሻል፤ አሁን እሱም የለም፣ እንደገና በበጐ ፈቃድ አገልግሎት እንደምትሳተፊ ሠምቻለሁ? እስቲ በዚህ ዙሪያ አውጊኝ… ከፊልሙ እንነሣ፡፡ “ሩሀማ” ፊልም ላይ ያው ሩሃማን ሆኜ ተጫውቻለሁ፡፡ ፊልሙን አይተሽው ከሆነ ሩሀማ በጣም የምታሣዝን ሴተኛ አዳሪ የነበረች ከዚያ የህይወት ብርሀን ያየችና ያ ብርሀን መልሶ የጠፋባት ሴት ናት፤ ጥሩ ተሳክቶልኝ ሠርቼዋለሁ፡፡ እኔ እንደዚህ አይነት ገፀ-ባህሪ አይከብደኝም፡፡ ለምን ብትይ በተፈጥሮዬ አልቃሻና ሆደ ባሻ ነኝ፡፡ ፊቴም ለዚያ አይነት ባህሪ ምቹ ስለሆነ መሠለኝ እዛ ቦታ ላይ የሚመድቡኝ፡ ፊልሙን ትተሽ “እርጂኝ አብሮ አደጌ”ን አስቢው፤ እዛ ላይ ተጨንቄ ፊቴ እንደሚያሣዝን ነው የሚታየው፡፡ “ሠካራሙ ፖስታ ላይም እንዲሁ አሳዛኝ ሴት ሆኜ ነው የሠራሁት፡፡ ይህቺ ሴት ኤች አይቪ በደምሽ ውስጥ አለ ተብላ፣ ራሷን ከማህበረሠቡ ለማግለል ገዳም የምትገባ ግን ከገዳም የሚመልሣት ሠው ያገኘች ሴት ናት፡፡ ሁሉም ላይ እንዲህ አሣዛኝ ክፍል ላይ ነው የሚመርጡኝ፡፡ ማስታወቂያን በተመለከተ ብዙ ባልገፋም ሞክሬያለሁ፡፡ ሁለት ወይ ሶስት ማስታወቂያ ነው የሠራሁት፡፡ አንዱ በፊት ነው፤ አለሙ ገ/አብ ነፍሱን ይማረውና መርጦኝ፣ ጋሽ ውብሸት ወርቅአለማሁ ጋ ለእንቁጣጣሽ በዓል ከጓደኞቼ ጋር ስንዘፍን፣ እኔ ከጐጆ ቤት ወጥቼ ሠንደል ሳጨስ እታያለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ ከሠራዊት ፍቅሬ ጋር አምባሣደር ልብስ ላይ ሠርቻለሁ፡፡ ብቻ ብዙ የሚወራለት አይደለም ማስታወቂያው፡፡ ፊልሙ አሁን ቆሟል፡፡ ብዙ ትኩረቴን ያደረግሁት አልበሙ ላይ ነው፡፡ በመሀልም ያው በስራ ምክንያት አሜሪካ ስድስት ወር እሠራለሁ፣ እመጣለሁ፡፡ እንደዚህ ሆነና ግጥም ዜማ ስሠበስብ በቃ ፊልሙ ተረሣ፤ ነገር ግን የመስራት ፍላጐት አለኝ፡፡ በጐ ፈቃደኝነትን በተመለከተ “እናት ለምን ትሙት” ዘመቻ ላይ “እችላለሁ” የሚል ዘፈን ሠርቻለሁ፡፡ ከሌሎችም አርቲስቶች ጋር የበጐ ፈቃድ ዘፈኖችን ሠርቻለሁ፡፡ ወደፊትም የበጐ ፈቃድ ሥራ የመስራት ፍላጐት አለኝ፡፡ አሁን በአልበሙ ስራ ሩጫ ላይ ስለሆንኩ እንጂ እቀጥላለሁ፡፡ በተለይ በትራፊክ ችግር፣ በእናቶች ሞት፣ በህፃናት መደፈርና በመሠል ማህበራዊ ችግሮች ላይ የመስራት ፍላጐት አለኝ፡፡ ከአልበሙ በኋላ እመለስበታለሁ፡፡ አሁን ወደ አዲሱ ሥራሽ እንምጣ በቅርቡ ከአሜሪካ የመጣሽው አዲስ አልበም ልታወጪ መሆኑን ሰምቻለሁ…

አዎ፡፡ አሜሪካ ስራ ላይ ነበርኩኝ፡፡ ከስራዬ ጐን ለጐን ለአልበሜ ግጥምና ዜማ እዛም ካሉ ባለሙያዎች ስሠበስብ ነበር፡፡ አሁን በጣም ጥሩ የሆነ የተለያየ ስብስብ፣ ባህልም ዘመናዊም፣ ጉራጊኛም ያካተተ ሥራ ሠርቻለሁ፡፡ ሠውም በጉጉት እንደሚጠብቅ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ የአልበምሽ መጠሪያ “የለሁበትም” ይሠኛል፡፡ ከምኑ ነው የሌለሽበት?

የለሁበትም እንግዲህ… አንቺ ከብዙ ነገር የለሁበትም ልትይ ትችያለሽ፤ ነገር ግን ይሄ ዘፈን የፍቅር ዘፈን ነው፡፡ ትክክለኛ ሀሣቡ በትዳር ወይም በጓደኝነት ብቻ በፍቅር ውስጥ ያለች ሴት ናት፡፡ ነገር ግን ባሏ ወይም ፍቅረኛዋ እሷን አይንከባከባትም፤ ጊዜ አይሠጣትም፤ ብቻ እንደ ፍቅረኛ ከጐኗ አይሆንም፡፡ የእሷን ድካም ፍቅር አይረዳም፤ ስለዚህ “እባክህ ከእኔ ጋር ከሆንክ አብረን ፍቅራችንን እናጠንክር፤ እምቢ ብለህ እኔ ሀሣቤን ብቀይር በኋላ የለሁበትም” በሚል ነው የምታስጠነቅቀው፡፡

አልበምሽ በዋናነት በምን ላይ ያተኩራል?

ሁሉንም ያካትታል፡፡ ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ ከከተማ እስከ ገጠር የሚዳስስ ነው፡፡ አሁን ስለ ገጠሩ ህይወት የሚዳስስ “ባጥ አሣቅሉኝ” (ጐጆ አቃልሱኝ) እንደማለት ነው፡፡ አይነት ደስ የሚል ዘፈን ሁሉ አለው፡፡ ይህ ዘፈን የአገሬው ሠው ሆ ብሎ ቤት እንዲያሳራት የምትማጠንበት ነው፡፡ ሁለት የሂሩት ዘፈኖች ተካተውበታል፣ “ተረት ተረት”፣ “ቸር ወሬ” የሚሉና ሌሎችም ምርጥ ምርጥ ዘፈኖች ተካተዋል፡፡ በአጠቃላይ 13 ያህል ዘፈኖች አሉት፡፡ አዲስ ሥራ ሲሠራ እነማን ተሳተፉ የሚል የተለመደ ጥያቄ አለ፡፡ አንባቢም ስለሚጠብቅ በግጥም፣ በዜማ፣ በቅንብር ማን ማን እንደተሳተፈ ንገሪኝ? ጌራወርቅ ነቃጥበብ፣ ተመስገን አፈወርቅ፣ አስቻለው ዲሮ በዜማ ተሣትፈዋል አብርሽም በግጥም ተሣትፏል፤ ሁለት ዜማም አለው፡፡ ሄኖክ ነጋሽ የሁለት ባህላዊ ዘፈኖች ዜማ ሠጥቶኛል፡፡ ደሣለኝ መርሻ የተሳተፈበት ጉራጊኛ አለኝ፡፡ የሂሩትን ሁለቱን ስሠራ አንዱ ላይ አርቲስት ተስፋዬ አበበ (ፋዘር) በግጥም ተሣትፎበታል፤ ሻምበል መኮንንም ተሣትፎ አድርጐበታል፡፡ ሌሎች ባለሙያዎች ተሣትፈዋል፡፡ ሌሎች ባለሙያዎችም ተሣትፈዋል፡፡ ቅንብሩስ…? ካሙዙ ካሣ አራት ዘፈኖችን፣ አስቻለው ዲሮ ሶስት፣ ሄኖክ ነጋሽ አንድ ዘፈን፣ እያሱ እስራኤል አለ፤ ተሾመ ጥላሁን፣ አሸብር ማሞ እና ኢዮብ ፋንታሁን ያቀናበሩት ሲሆን ሚክሲንጉን አስቻለው ዲሮ ሠርቶታል፡፡ በአጠቃላይ ብዙ ደክሜበታለሁ፡፡ ወጪውም ወገቤን የሚያሠኝ ነው፡፡ ከወጪው ባሻገር ከተለያየ ባለሙያ ጋር ሲሠራ ብዙ ስሜቶችን አስተናግዶ፣ ታግሶ ማለፍ አስፈላጊ በመሆኑ ፈታኝ ነበር፡፡ አሜሪካ ሲሄድ ስመጣ ብቻ ወደ ሁለት ዓመት ፈጅቷል፡፡ ገንዘቡ፣ ጉልበት፣ የሠዎች ትብብር ሳይጨመር እንኳን ከባድ ነው፡፡ አሁንም ወጪ ላይ ስለሆንኩ ይሄን ያህል አውጥቼአለሁ ልልሽ ግን አልችልም፡፡ የማሣትመውም ራሴ ነኝ፡፡ ኮከብ ሙዚቃ ቤት ለማከፋፈል ስምምነት አለን፡፡

መቼ እንጠብቅ?

እኛ እግዜር ከፈቀደ ለፋሲካ ብለናል፡፡ በሩጫ ላይ ነን፡፡ እንግዲህ ማስተሪንግ የምናሠራባቸው ህንዶች ሠሞኑን ሲዲ አልቆብናል ብለውናል፤ ግን አሁን እናስመጣለን ብለዋል፡፡ እሱ ካለቀልን ለፋሲካ አሪፍ ስራ እናበረክታለን፡፡ ለአንዳንዶቹም ዘፈኖች ክሊፕ እየሠራሁ ነው፡፡ ከስራሽ ወጣ እንበልና ስለ አንቺና ስለ ባለቤትሽ አብርሀም (አብርሽ ዘጌት) ትንሽ እናውራ ይቻላል፡፡ በፊት ጥሩ ወንድምና እህት ሆናችሁ፤ ረጅም ጊዜ ቆይታችሁ በሠዎች ወሬ ባልና ሚስት ሆናችሁ ይባላል፡፡ እንደውም “ወሬውን ሠምቻለሁ” የተባለው ነጠላ ዜማሽ የተዘፈነው ከዚሁ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ነው ይባላል፡፡ ምን ያህል እውነት ነው? እንዳልሽው እኔ እና አብሪ ግንኙነታችን ክለብ ውስጥ ነው፡፡ እኔም ልዘፍን እሱም ሊዘፍን መጥቶ ማለት ነው፡፡ የሚገርምሽ ግን ሁለታችንም የፈረንሳይ ልጆች ሆነን ግን አንተዋወቅም ነበር፡፡ እሱ የአቦ ሠፈር ልጅ ነው፤ እኔ 07 ቀበሌ ነኝ ግን አንተዋወቅም፡፡ ካዛንቺስ “አልማዝ ላሊበላ” የተባለ ክለብ ነው የተገናኘነው፡፡ ከዚያ ሌሎች ቤቶችም አብረን በመስራት በወንድምነትና እህትነት ረጅም የጓደኝነት ጉዞ አድርገናል፡፡

ግን የሆነ ሠዓት ላይ ዝም ብለን ትዳር አደረግነው እና ህይወት ቀጠለ፡፡ የጠበሠም የተጠበሠም የለም እያልሽኝ ነው? (ሣ…ቅ) አዎ የጠበሰም የተጠበሠም፣ የጠየቀም የተጠየቀም የለም፡፡ እኛ ከፍቅር ግንኙነት ውጭ በጣም ጓደኛሞች ሆነን ስንኖር ሠዎች ዝም ብለው ያወሩ ነበር፡፡ ይሄም አንድ ምክንያት ነበር፡፡ እንዳልሽው “ወሬውን ሠምቻለሁ አሜን ይሁን ብያለሁ” የተሠኘው ነጠላ ዜማም ከዚሁ ጋር ግንኙነት አለው፡፡ ሠርግም ግርግርም የለም፤ ከዚያ ክርስቲያን አብርሀም ተወለደች፤ እሷው አጋባችን፡፡ አሁን አምስት አመት ሞላት፡፡ ለክርስቲያን ወንድምና እህት አልሠጣችኋትም? አዎ ገና አልመጣም፡፡ ምክንያቱም ሩጫው ትኩረት እንድንሠጥ አላደረገንም እና አላሠብንበትም፡፡ ተወልደሽ ያደግሽው እውቁ አትሌት ዋቢ ቢራቱ ሠፈር በመሆኑ ሯጭ ትሆኛለች ተብሎ ሲጠበቅ አንቺ ዘፋኝ ሆነሽ አረፍሽው… በመሠረቱ ከፈረንሳይ ብዙ ጥበበኞች ወጥተዋል፡፡ ሁሌ “ከውሀው ነው መሠለኝ” እንላለን፡፡ ትንሿ የኢትዮጵያ ሆሊውድም ትባላለች፡፡ ከያኒ፣ ጋዜጠኛ፣ ሯጭ ብቻ ጥበበኞች አሏት ፈረንሳይ፡፡ እኔ እንደ ዋሚ ቢራቱ ሯጭ ባልሆንም ዘፋኝ ሆኛለሁ ለማለት ነው፡፡ በመጨረሻ ከ “የለሁበትም” አልበምሽ ምን ትጠብቂያለሽ? እኔ ጥሩ ነገር እጠብቃለሁ፡፡ ሁሉንም ያማከለ ስራ ነውና፡፡ ወጣቱም ጐልማሣውም ሊያዳምጠው የሚችለው ስራ ነው፡፡ ከእኔ ጋር ብዙ የደከሙ ባለሙያዎች፣ ጓደኞች፣ ባለቤቴ አብርሽ በጣም ሊመሠገኑ ይገባል፡፡ ቢጂ አይ ኢትዮጵያንም አመሠግናለሁ፡፡ እና አሪፍ ነገር አለ ብዬ ነው የምጠብቀው፡፡ “አንቺ የለሁበትም” እንዳልሽው፣ አልበምሽን አሪፍ አድርገሽ ባታመጪ “እኛም የለንበትም”… አብረን የምናየው ይሆናል፡፡ በጣም አመሠግናለሁ ሙናና፡፡ እኔም ከልብ አመሠግናለሁ፡፡

Saturday, 20 April 2013 12:44

ቀረች ቢሉኝ

ለካ ከልቤ እወድሽ ነበር
ለካስ ከልቤ አፈቅርሻለሁ
ከእውነት እንደማስብሽ
ከአንጀቴ እንደናፈቅኩሽ
ዛሬን ለኔ አውቄዋለሁ፡፡
ዛሬን ነገን ትመጪ እያልኩ
ቀን ስቆጥር እየኖርኩኝ…
አንቺን ከማሰቤ ጋር
አንቺን ከናፍቆቴ ጋር
እያሰብኩሽ እያለምኩ
መልክሽን ይዤ እየዋልኩ
ሰውነትሽን ይዤ እያቀፍኩ
ሳወራልሽ እያደርኩኝ…
ዛሬ ነገ ላገኝሽ
ቀኔን ስቆጥር እየኖርኩኝ
ቀረች ቢሉኝ
መቼ ደርሰሽ
መች አግኝቼሽ
የልቤን ቃል
ላጫውትሽ፡፡
እስክትመጪ አጠራቅሜ
አስቀምጬ ያቆየሁሽን
የፍቅራችንን ምስጢር
ተቃቅፈን “ምናወራትን
ምንንሾካሾካትን
መቼ ደርሰሽ እያልኩ እኔ
ቀኑ ረዝሞ ሌ ቱ ጨንቆኝ
ላንቺ ብዬ ተካፍዬ
ለሌላ የማልነግረውን
ጭንቀቴን ሃሳቤን ሁሉ
ሳሰላስል የኖርኩትን
ሳላዋይሽ ቀረች ቢሉኝ
ምን ሊውጠኝ?
ታህሳስ 18/1980
(“ሶረኔ” ልዩ ልዩ የበረሃ ግጥሞች
ከሚለው መድበል የተወሰደ)

በር አባ ዳዊት ወርቁ የተፃፈው “The Ethics of Zara Yacob” እንዲሁም በአባ ብሩክ ወልደገብር እና አባ ማርዮ አሌክሲስ ፓርቴላ የተዘጋጀው “Abyssinian Christianity. The First Christian Nation?” መጽሐፍ በመጪው ረቡዕ እንደሚመረቁ የቅዱስ ቶማስ አኩዊናስ የኢትዮጵያ ካቶሊክ ዩኒቨርሲቲ አስታወቀ፡፡ የሁለቱ መጻሕፍት ማስተዋወቂያ ዝግጅት የሚካሄደው አስኮ በሚገኘው የቅዱስ ፍራንሲስ ካቶሊክ ገዳም ካፑቺን ፍራንሲስ የጥናትና ሥልጠና ማእከል አዳራሽ ነው እንደሚከናወን ታውቋል፡፡

ኢትዮጵያን ለሚጐበኙ የውጭ ሀገር ጐብኚዎች የሚያገለግል የመምሪያ መጽሐፍ አሳትሞ ማሰራጨት መጀመሩን “ኬር ኤዢ ኢትዮጵያ” አስታወቀ፡፡ በእንግሊዝኛ እና በእስፓኒሽ ቋንቋ የታተመው የጐብኚዎች መምሪያ መጽሐፍ ግማሽ ሚሊዬን ብር ወጥቶበታል ያሉት አዘጋጆቹ፤ መጽሐፉ ኢንዱስትሪውን ቢያነቃቃም በውጭ ሀገር ታትሞ ወደሀገር ሲገባ የመንግስት ተቋማት አላበረታቱንም ብለዋል፡፡ አብዛኞቹን ማስታወቂያዎችም በነፃ ያሳተሙ መሆናቸውን ለዝግጅት ክፍላችን ተናግረዋል፡፡

በwww.ker_ezhiethiopia.com የሚገኘው መጽሔት 20ሺህ ቅጂ የታተመ ሲሆን ቅጂው ከራስ ሆቴል እና ሌሎች ትልልቅ ሆቴሎች በነፃ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡

ላፍቶ ጋለሪ ከአርባ በላይ የሴት ሰዓሊያን ሥራዎችን ያካተተ “Inspired women2” የተሰኘ የስዕል አውደርዕይ ከትላንት በስቲያ ለተመልካች ማቅረብ ጀመረ፡፡ ኢትዮጵያውያንና የውጭ አገር ሴት ሰዓሊያን የተሳተፉበት አውደርዕይ ከ150 በላይ የስዕል ስራዎች የያዘ ሲሆን ለአንድ ወር ለህዝብ ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ታውቋል፡፡

በአንጋፋው ደራሲ ኃይለመለኮት መዋዕል የተዘጋጀ “እንካስላንቲያ” የተሰኘ መፅሃፍ ሰሞኑን ለንባብ ቀረበ፡፡ ደራሲው ስለ መፅሃፉ ፋይዳ በገለፀበት መግቢያ፤ “የእንካስላንቲያ ሥነ-ቃል የግጥማዊ ዜማነት ባህሪይ ስላለው ወጣቶች እየተፈራረቁና እየተፎካከሩ በመሳተፍ አያሌ ቁምነገሮችን … ይማሩበታል” ብሏል፡፡

በ107 ገፆች የተቀነበበው መፅሃፉ፤ ዕውቀት፣ ዲሞክራሲ፣ ሙስና፣ ፍትህ ወዘተ በሚሉ ርዕሶች ስር የተዘጋጁ እንካስላንቲያዎችን የያዘ ሲሆን በ20 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ኃይለመለኮት መዋዕል “ጉንጉን” እና “የወዲያነሸ” በተባሉት ተወዳጅ የረዥም ልብወለድ ሥራዎቹ ይታወቃል፡፡

ባለፈው ሚያዝያ 2 መቅረብ የነበረበትና ታዳሚዎች በሥፍራው ከተገኙ በኋላ የተቋረጠው “ግጥም በጃዝ” በመጪው ረቡዕ እንደሚቀጥል አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ ቅድመ ዝግጅት አጠናቀን ልናቀርብ ከተዘጋጀን በኋላ የቂርቆስ ክፍለ ከተማ ተቆጣጣሪ አካል ፈቃድ የላቸውም በማለቱ ስለሌላቸው አያቀርቡም በሚል ለራስ ሆቴል ዝግጅቱ መቋረጡን ተናግረዋል፡፡ ረቡዕ ከቀኑ 11 ሰዓት በሚቀጥለው “21ኛው ግጥምን በጃዝ” ዝግጅት ላይ ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ፣ ሞገስ ሀብቱ፣ ምስራቅ ተረፈ፣ በረከት በላይነህ፣ ግሩም ዘነበ በግጥም፤ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በወግ ይሳተፋሉ፡፡

Saturday, 20 April 2013 12:16

የሕይወት ስንቅ

        ከ1/3ኛ በላይ የህፃናት ሞትን በክትባት መከላከል ይቻላል

የፈንጣጣ በሽታ በኢትዮጵያ መኖሩ በታወቀ ጊዜ ከፓሪስ የህክምና ፋኩሊቲ የተውጣጡ ቡድኖች ህዝቡን ለመከተብ በሚል በ1890 ዓ.ም አዲስ አበባ ገቡ፡፡ ያኔ ህብረተሰቡ ስለ ፈንጣጣ በሽታም ሆነ ስለሚሰጠው ክትባት ምንም ግንዛቤ ስላልነበረው፣ ክትባቱን ለመውሰድ ፈቃደኛ አልነበረም፡፡ ይህንን ሁኔታ ለመቀየርና ህዝቡን ለመቀስቀስ አጤ ሚኒልክ የፈንጣጣውን ክትባት በፈረንሳዮች እጅ ተከተቡ። ይህ ሁኔታ ግን የክትባትን ጠቀሜታ ህብረተሰቡ በአግባቡ እንዲረዳና ክትባቱን ለመውሰድ ፈቃደኛ እንዲሆን ባለማድረጉ ንጉሱ አዋጅ አስነገሩ፡፡ “አሁን በከተማው ፈንጣጣ ገብታ ሰውን ሁሉ እንደምትፈጅ ታያላችሁ፡፡

ይህቺንም ክፉ በሽታ ከአገር ለማጥፋት በከተማ ያለው ሰው አዋቂውም ልጁም ከከብት ሃኪም ዘንድ ወይም ከሆስፒታል እየሄደ ይከተብ፡፡ ለመከተብ ዋጋ አያስከፍልም። ጊዜም አያስፈታ፡፡ ከአምስት ደቂቃም ይበልጥ አያቆይ፡፡ አሁንም ለራሳችሁና ለልጆቻችሁ የምታስቡ ሰዎች ሁሉ ተከተቡ፡፡ ሳትከተቡ ቀርታችሁ ሰው ቢሞትባችሁ በስንፍናችሁ መሆኑን እወቁት” ይህ የአጤ ሚኒሊክ አዋጅ መጋቢት 2ቀን 1904 ዓ.ም በገበያ መሃል እንዲነበብ ተደረገ፡፡ በማግስቱ በርካታ ቁጥር ያላቸው ሰዎች ውርዝ እየተባለ በሚጠራውና በወቅቱ ክትባቱን ይሰጥ በነበረው ሐኪም መኖሪያ ቤትና የሥራ ቦታ ይሰባሰቡ ጀመር፡፡ ስለሁኔታው ውርዝ የተባለው ይኸው ፈረንሳዊ ሐኪም ሲናገር፤ “አዋጁ በተነበበ ማግስት ከተለያዩ አቅጣጫዎች በርካታ ሰዎች ወደ ቤቴ ይመጡ ጀመር፡፡ የአምስትና የስድስት ቀናት ጉዞ አድርገው አዲስ አበባ የሚመጡት ሰዎች ተራ ደርሷቸው እስኪከተቡ ድረስ በቤቴ አካባቢ በመስፈራቸው በራፌ ላይ ዘብ አቆምኩ፡፡ ከየካቲት ወር እስከ ነሐሴ ድረስም 20ሺ 700 ሰዎችን አዲስ አበባ ውስጥ ከተብን” ማለቱን ጳውሎስ ኞኞ “አጤ ሚኒልክ” በተሰኘው መፅሃፉ ላይ አስፍሮታል፡፡ በኢትዮጵያ ዘመናዊ የክትባት ታሪክም በአፄ ሚኒልክ ዘመነ መንግሥት የተሰጠው ክትባት የመጀመሪያ ነው፡፡

ክትባቶች በተለያዩ አይነቶች ተዘጋጅተው ወደሰውነታችን እንዲገቡ ከተደረጉ በኋላ የሰውነታችንን በሽታ የመከላከል አቋም (“Immunity”) የሚያሳድጉ የህክምና ጥበቦች ናቸው፡፡ እ.ኤ.አ በ1769 ዓ.ም ኤድዋርድ ጅነር በተባለ ሰው አማካይነት ለመጀመሪያ ጊዜ በጥቅም ላይ የዋለው ክትባት የተሰራው ከከብት ቫይረስ እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ይህ ከከብት ቫይረስ ተሰርቶ ጥቅም ላይ መዋል የጀመረው ክትባት፤ በየጊዜው የተለያዩ ለውጦችንና መሻሻሎችን እያሳየ በመሄድ ዛሬ ከደረሰበት ደረጃ ላይ ሊደርስ ችሏል፡፡ ክትባቶች አይነታቸውም ሆነ መጠናቸው የተለያየ ሲሆን የአሰጣጥ ሂደታቸውም ክትባቱን የሚወስደውን ሰው እድሜ መሰረት ያደረገ ነው፡፡ የአለም ሀገራት ህዝባቸውን መሰረት ባደረገ መልኩ ለክትባት አመራረትም ሆነ አሰጣጥ ፖሊሲዎችን ያረቃሉ፡፡ በተለያዩ ህጐች፣ መመሪያዎችና ደንቦች መሰረትም ሊመሩ ይችላሉ፡፡ በዓለም አቀፍ ስምምነቶች መሰረት ግን እነዚህ ፖሊሲዎችና መመሪያዎች የትኛውንም ህዝብ የክትባቱ ተጠቃሚ እንደሚያደርጉ ማረጋገጥ ይጠበቅባቸዋል፡፡

ለኩፍኝ፣ ለፖሊዮ፣ ለመንጋጋ ቆልፍና ዘጊ አናዳ የመሳሰሉትን በሽታዎች ለመከላከል የሚሰጡት ክትባቶች፣ የአለም ህዝቦችን አስከፊ ወደሆነ የወረርሽኝ ጥቃት እንዳይገቡ ትልቅ ጠቀሜታ ይኖራቸዋል ተብሎ ይታመናል፡፡ ኢትዮጵያ የክትባት አገልግሎትን ለህዝቦቻቸው ለማዳረስ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ ከሚገኙ የአለም አገራት መካከል አንዷ ናት፡፡ በአገሪቱ ከሚከሰቱት የህፃናት ህመምና ሞት መካከል አንድ ሶስተኛው የሚሆኑት በክትባት መከላከል በሚቻል በሽታዎች አማካይነት የሚፈጠሩ ናቸው፡፡ ህብረተሰቡ በክትባት ላይ ያለው ግንዛቤ አነስተኛ በመሆኑና አገልግሎቱም በአስተማማኝና በበቂ መጠን ባለመዳረሱ ምክንያት ዛሬም ድረስ በርካታ ህፃናት በክትባት ሊወገዱ በሚችሉ በሽታዎች እየተጠቁ ለህመም፣ ለአካል ጉዳትና ለሞት ሲጋለጡ ይስተዋላል፡፡ “ህፃናትን በማስከተብ ከህመም፣ ከአካል ጉዳትና ከሞት እንጠብቃቸው” በሚል መሪ ቃል ከሚያዝያ 14-20 ቀን 2005 ዓ.ም በአገራችን ለሦስተኛ ጊዜ የሚከበረውን የአፍሪካ የክትባት ሳምንት አስመልክቶ የፌደራል ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ሰሞኑን በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፤ አገሪቱ ክትባትን ለህብረተሰቡ ሁሉ በበቂ መጠን ለማዳረስ ጥረት እያደረገች ነው፡፡

የክትባት ሽፋኑና አገልግሎቱ በአስተማማኝነት ያደገና የጉዳት መጠኑ የቀነሰ ቢሆንም በየደረጃው ያለው የህብረተሰቡ ግንዛቤ ባለማደጉ ምክንያት በክትባት ሊወገዱ የሚችሉ በሽታዎች በርካታ ህፃናትን ለአካል ጉዳትና ለሞት እያጋለጡ ይገኛሉ፡፡ ሚኒስትር መ/ቤቱ እንደ ኩፍኝ የመሳሰሉ ወረርሽኞችን ለማስቆም፣ በሁሉም የጤና ድርጅቶች ያለምንም ክፍያ ክትባትን ለህፃናት በማዳረስ ላይ መሆኑንም በዚሁ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ አስታውቋል። በአገሪቱ የሚገኙት ከ250 በላይ ሆስፒታሎች፣ 3ሺህ ጤና ጣቢያዎችና 25ሺ ጤና ኬላዎች ክትባትን ለህብረተሰቡ በማዳረሱ ረገድ ቁልፍ ሚና እንዳላቸውም በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተሩ አቶ አህመድ ኢማም ተናግረዋል፡፡ የአገሪቱ የመደበኛ ክትባት ፕሮግራም ሽፋን እ.ኤ.አ በ2003 ከነበረበት 52 በመቶ እድገት አሳይቶ 86 በመቶ መድረሱንም ጋዜጣዊ መግለጫው ይፋ አድርጓል፡፡ የበሽታዎችን ስርጭት በቀላሉ ለመቆጣጠርና ጤናማ ትውልድ ለማፍራት ትልቅ ጠቀሜታ አለው የሚባለውን የክትባት አገልግሎት ስርጭትና ጥራት በተመለከተ ለግንዛቤ የሚረዱ አንዳንድ መረጃዎችን በሥራ አጋጣሚ በተዘዋወርንባቸው አካባቢዎች ለማሰባሰብ ሞክረን ነበር፡፡ በሐረርጌ ዞን አፈር ደባ ሶፊ ወረዳ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ያገኘኋት የአምስት ልጆች እናት፣ የ39 አመቷ ዘሀራ የሱፍ የወለደቻቸው አምስቱም ልጆቿ ክትባት አለመከተባቸውንና ልጆቿን ለማስከተብ የሚያስችል ገንዘብ እንደሌላት ነግራኛለች።

ክትባቱ በሁሉም የጤና ጣቢያዎችና የጤና ኬላዎች ያለክፍያ እንደሚሰጥ የሰማሁትን ብነግራትም በጄ አላለችኝም፡፡ “የእከሌ ልጅ አልተከተበችም፣ እከሌም ልጇን አላስከተበችም፡፡ ግን ምንም አልሆኑባትም፡፡ ለምን አስከትባለሁ” መልሳ ጠየቀችኝ፡፡ ክትባት ለወደፊቱ የልጆቿ ጤናማ ህይወት መሰረት መሆኑንና በወረርሽኝ መልክ ከሚከሰቱ በሽታዎች በቀላሉ መዳን እንደሚቻል ብነግራትም ሃሳቤ ሊዋጥላት አልቻለም፡፡ ይሄ የሚያሳየው በጤናው ዘርፍ የሚሰሩ መንግሥታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የህብረተሰቡን ግንዛቤ ለማሳደግ በበቂ ሁኔታ አለመንቀሳቀሳቸውን ይመስለኛል፡፡ በምዕተ አመቱ የልማት ግብ ተደርገው ከተያዙት ጉዳዮች መካከል አንዱ የሆነውና እድሜያቸው ከአምስት አመት በታች የሆኑ ህፃናትን ሞት መቀነስ የሚለውን ጉዳይ ለማሳካት ሁሉም በዘርፉ የሚንቀሳቀሱ ባለድርሻ አካላት ብዙ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ክትባቶች በበቂ ሁኔታ መሰራጨታቸውን ብቻ ሳይሆን፣ ህብረተሰቡ ስለ ክትባት ጠቀሜታ በአግባቡ ተረድቶ በጊዜውና በወቅቱ ልጆቹን እንዲያስከትብ ለማድረግ በመጀመርያ ግንዛቤውን ማሳደግ ዋንኛ ተግባር ነው። ከዚህ በተጨማሪም ለህብረተሰቡ እንዲደረሱ በየአካባቢው የሚሰራጩት ክትባቶች ጥራትና ወደ ተጠቃሚው የሚደርሱበት ሁኔታ ምን ያህል አስተማማኝ ነው የሚለውን ማየትም ግድ ይላል፡፡

በጥንቃቄ ጉድለት የተበላሹ ክትባቶች ከጥቅማቸው ጉዳታቸው ያመዝናልና ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ ክትባቶች ከተመረቱበት ቦታ ጀምሮ ወደ ተጠቃሚው እስከሚደርሱበት ጊዜ ድረስ ያለው ሂደት ቀዝቃዛው ሰንሰለት (Cold chain) በሚል መጠሪያ ይታወቃል፡፡ ክትባቱ ተመርቶ ውጤታማ የሆነ አገልግሎት እንዲሰጥ ለማድረግም፣ ይህ ሰንሰለት ሂደቱን ጠብቆ በአግባቡ ተግባራዊ መደረግ ይኖርበታል፡፡ ቀዝቃዛውን ሰንሰለት መሰረት ባደረገ መልኩ ጥቅም ላይ ያልዋለ ክትባት መድሃኒትነቱ አስተማማኝ አይሆንም፡፡ የማቀዝቀዣ እጦት በድሃ አገራት ክትባትን በበቂ መጠን ለማዳረስ ትልቅ እንቅፋት ሲሆን የሚስተዋለውም ለዚህ ነው፡፡ ይህንን ችግር ለማስወገድና ያለፍሪጅ በመቆየትና ከቦታ ቦታ በመዘዋወር አገልግሎት ላይ ለመዋል የሚችሉ ክትባቶችን ለማምረት ሳይንቲስቶች ከመትጋት አልቦዘኑም፡፡ ሔፒታይተስ ቢ የተባለውን ገዳይ በሽታ ለመከላከል ያስችላል የተባለውን ክትባትም በድንች ዘሮች ውስጥ በማስገባትና በማምረት ለምግብነት ማዋል ጀምረዋል፡፡ እነዚህን ድንቾች በተመገቡ ሰዎች ላይ በተደረገ ጥናት መሰረትም 60 በመቶ የሚሆኑት የድንቹ ተመጋቢዎች ሔፒታይተስ ቢ የተባለውን በሽታ ለመከላከል የሚያስችላቸው (Anti Bodies) በደማቸው ውስጥ ተገኝቷል፡፡

ይሁን እንጂ ሳይንቲስቶቹ እነዚህን ክትባት የያዙ ድንቾችን በስፋት ለማምረትና ለማሰራጨት እንቅፋት ይሆናሉ የሚሏቸው ችግሮችም አሉ፡፡ ከእነዚህ መካከልም የአወሳሰድ መጠኑ (Dosage) አለመመጠን አንዱ ሲሆን ሌላው ደግሞ ድንቾቹ ከሌሎች ለምግብነት ከሚውሉ ድንቾች ጋር ተቀላቅለው ለተራ ምግብነት ሊውሉ ይችላሉ የሚለው ስጋት ነው፡፡ ያም ሆነ ይህ በሚበሉ ምግቦች መልክ እየተዘጋጁ ጥቅም ላይ እንዲውሉ የሚደረጉት የክትባት አይነቶች እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ድሃ አገራት ውስጥ ክትባትን ለማዳረስ እንቅፋት የሆነውን የፍሪጅ አገልግሎት ለማስቀረት ትልቅ ጠቀሜታ ይኖራቸዋል፡፡ የፌደራል ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፣ አሁን በአገሪቱ እየተሰጡ ያሉትን ዘጠኝ አይነት ክትባቶች በቁጥር ከፍ ለማድረግ ጥረት በማድረግ ላይ እንደሚገኝም አስታውቋል፡፡ አሁን በአገሪቱ በስፋት እየተሰጡ ከሚገኙ የክትባት አይነቶች መካከል ፖሊዮ፣ ኩፍኝ፣ መንጋጋ ቆልፍ፣ ዘጊ አናዳ፣ ማኔንጃይትስና ሔፒታይተስ ቢ ጥቂቶቹ ናቸው፡፡

(ስለምርጫው የተሰጠ አስተያየት)

እንካ ስላንቲያ?

በምንቲያ?

በረገጣ! ምናለ በረገጣ?

በህዝባዊ አመራር መድበል ካላመጣ እያደር ይፋጃል ያንድ ፓርቲ ጣጣ!! ሰሞኑን እጄ የገባው መፅሃፍ ለየት ያለ ነው፡፡ ከአሁን ቀደም እንዲህ ያለ መፅሃፍ መውጣቱን አላውቅም፡፡ “እንካስላንቲያ” ይላል የመፅሃፉ ርዕስ፡፡ ደራሲው ግን ዝነኛ ነው፡፡ “ጉንጉን” እና “የወዲያነሽ” በተባሉት ወርቅ የልብወለድ ሥራዎቹ ይታወቃል፡፡ አንጋፋው ደራሲ ኃይለመለኮት መዋዕል! እኔማ እንዴት አሰበው አስብሎኛል፡፡ ቁጭ ብሎ እንካ ስላንቲያ መፍጠር እኮ ቀልድ አይደለም፡፡ ትዕግስት ይጠይቃል፡፡ በዚያ ላይ የመረጣቸው ርዕሰ ጉዳዮች ከበድ የሚሉ ናቸው፡፡ እስኪ አስቡት --- ዕውቀት፣ዲሞክራሲ፣ ህዝብ፣ ፍትህ፣ የህግ የበላይነት፣ ሙስና ወዘተ … ርዕሶች ላይ ያተኮሩ እንካስላንቲያዎቿን ነው ያዘጋጀው፡፡ መፅሃፉን እየኮመኮምኩ ሳለ አንድ ሃሳብ ብልጭ አለልኝ፡፡ ሃሳቡ ለማን መሰላችሁ የሚጠቅመው? ለኢቴቪ ነው! እናላችሁ --- ኢቴቪ ለምን “የእንካስላንቲያ ውድድር” አያካሂድም ብዬ አሰብኩ፡፡ ፕሮፓጋንዳውንም ቢሆን እኮ በእንካስላንቲያ አጣፍጦ ቢያቀርብልን ይሻለናል!! በዛውም ትንሽ ብንዝናና ምናለበት፡፡ በነገራችሁ ላይ የፖለቲካ ፓርቲዎችም ቢሆኑ የምርጫ ክርክር ሲያካሂዱ በእንካስላንቲያ ቢያደርጉልን ሳይሻለን አይቀርም (ምርጫው የታለና እንዳትሉኝ ብቻ!) በተለይ እንዳሁኑ ኢህአዴግ ያመዘነበት ምርጫ ሲሆን እንካስላንቲያው ሞቅ ደመቅ የሚያደርገው ይመስለኛል፡፡ (ፓርላማውንም ምርጫውንም ተቆጣጠረው አይደል?) ከሁሉም በላይ ደግሞ ከ97 ምርጫ ወዲህ ጥቅልል ብሎ የተኛውን ፖለቲካችንን ከእንቅልፉ ለመቀስቀስም ማለፊያ ዘዴ ይመስለኛል - ፖለቲካን በእንካስላንቲያ ማስኬድ! ወጋችንም እንደ ዘንድሮ ምርጫና ፖለቲካ ጭር እንዳይል … ለምን በጥቂት እንካስላንቲያዎች ሞቅ ደመቅ አናደርገውም - እድሜ ለደራሲ ኃይለመለኮት!

እንካስላንቲያ?

በምንቲያ?

በወለምዘለም!

ምን አለህ በወለምዘለም?

አንጠርጥረህ ምረጥ በምርጫ ቀልድ የለም፡፡ አያችሁልኝ … ምርጥ የምርጫ ማስታወቂያ! ትንሽ ዘገየ እንጂ የአዲስ አበባ መስተዳድር ይጠቀምበት ነበር፡፡ በቅርቡ ሲያቀርበው የነበረው ግን ግግም ያለ ነው - እንድ ድራማቸው! ባይገርማችሁ የመስተዳደሩ ድራማ እኮ ልማታዊ ሳይሆን ፕሮፓጋንዳዊ ነው - በቃ ደረቅ- ችኮ - “እንጨት እንጨት” የሚል፡፡ የእንካስላንቲያው ግን ሌላው ቢቀር ያዝናናል፡፡ ሌላ ደግሞ ይሄውላችሁ - እንካስላንቲያ? በምንቲያ? በአምሮት! ምን አለህ በአምሮት? ሥልጣን ለሰጠህ ህዝብ ይኑርህ አክብሮት፡፡ አሪፍ መልዕክትና ቁም ነገር ይዛለች አይደል? ማንን እንደሚመለከት መግለፅ ግን አስፈላጊ አይመስለኝም (ግልፅ ነዋ!) እስቲ ደግሞ በመልካም አስተዳደር ዙርያ ደራሲው የፈጠረውን እንካ ስላንቲያ እንይ፡- እንካስላንቲያ? በምንቲያ? በመምጠቅ! ምን አለህ በመምጠቅ? መልካም አስተዳደር እንዳለ ለማወቅ ባለሥልጣን ሳይሆን ሕዝብን ነው መጠየቅ፡፡

ልክ ብሏል! በተለይ ኢቴቪ እቺን ቢሰማ ይጠቅመዋል፡፡ በቃ በልኩ የተሰፋች ናት! ራሱ ኢህአዴግ በ9ኛው ጉባኤ የመልካም አስተዳደር ችግር እንዳለ የተረዳው፣ከህዝቡ ምሬት እንደሆነ በግልፅ ተናግሯል እኮ፡፡ ኢቴቪ ግን ሁሌም ባለስልጣናትን ነው የሚጠይቀው፡፡ ምናልባት ወደፊት ግን ከኢህአዴግ ይማራል ብለን ተስፋ እናደርጋለን (አበሻ ተስፋ አይቆርጥማ!) እኔ የምላችሁ … የሰሞኑ ምርጫ እንዴት ነው? መረጣችሁ ወይስ ተመረጣችሁ? አንዱ ወዳጄ ምን አለኝ መሰላችሁ … “ምርጫ ድሮ ቀረ!” (የፈረደበትን የ97 ምርጫ ማለቱ እኮ ነው) ወዳጄ እርሙን አላወጣ ብሎኝ ነው እንጂ … ነግሬው ነበር እኮ! “እንደዛ ዓይነቱን ምርጫ ኢህአዴግ ዓይኑ እያየ አይደግመውም” ብዬ! (የለየለት ሞኝ አደረገው እንዴ?) ባለፈው ሳምንት የመኢአድ ሊቀመንበር ያሉት ግን ትንሽ ከበድ ይላል፡፡

አሁንም መኢአድ አለ እንዴ? (ይሁና!) እናላችሁ --- ስለምርጫው ተጠይቀው ኢንጂነር ኃይሉ እንዲህ አሉ “ይሄ ምርጫ ሳይሆን ንጥቂያ ነው!” እንዴት ቢማረሩ ነው ባካችሁ! ከምርጫው ራሱን ያገለለው የ33ቱ ፓርቲዎች ቡድን (ስም አልወጣለትም አይደል?) ምን ነበር ያለው? “ኢህአዴግን ለማጀብ ወደምርጫው አንገባም!” ብለው ነበር (ምን ያድርጉ? ምህዳር የለማ!) ባለፈው ሳምንት ከምርጫው በኋላ የምርጫ ቦርድ ሃላፊው ምን አሉ መሰላችሁ? (እኚህ እንኳን ፓርቲዎችን ሁሉ እንደልጆቼ ነው የማየው ያሉት) “እንዳሁኑ ምርጫ ፓርቲዎች ሳይወዛገቡ በሰላም የተጠናቀቀበት ጊዜ የለም” ይሄን የሰማ የቀድሞ የኢህአዴግ ደጋፊ ወዳጄ (አሁን ሃይማኖተኛ ሆኗል) “እውነታቸውን እኮ ነው … በምርጫው አልተሳተፉማ!” ብሎ እርፍ አለ! (ሰው ሁሉ በቀጥታ መናገር ተወ ማለት ነው?) እኔ ደግሞ ያስገረመኝ የአንዳንድ መራጮችና ተመራጮች አስተያየት ነው፡፡

ባለፈው እሁድ አንዱ መራጭ ድምጽ ሰጥቶ ሲወጣ የኢቴቪ ጋዜጠኛ ያገኘውና “ምርጫው እንዴት ነበር?” ይለዋል፡፡ (ኢንተርቪው በጥቆማ ነው የሚባለው ውሸት ነው አይደል?) መራጩም - “የመብራት ችግር አለ፣ የውሃ ችግር አለ፣ የመሰረተ ልማት ችግር አለ፣ በአጠቃላይ ብዙ ችግሮች አሉ፡፡ እነዚህን ችግሮች የሚፈታልኝን መርጫለሁ” (ማንን ይሆን?) ኢቴቪ ያነጋገራቸውን አስተያየት ሰጪዎች እንደኔ በቅጡ ሰምታችኋቸው እንደሆነ አላውቅም፡፡ “የመረጥኩት ኢህአዴግን ነው” ማለት እኮ ነው የሚቀራቸው፡፡ (ነግረውን ቢለይላቸው ይሻል ነበር!) ሌላ መራጭ ደግሞ እንዲህ አለ - በፈረደበት አንድ ለእናቱ ኢቴቪያችን፡፡ “ምርጫው ዲሞክራሲያዊና ፍትሃዊ እንዲሁም ልማታዊ ነው ማለት ይቻላል” አይገርምም… ልማታዊ ምርጫ! ኢህአዴግ ራሱ እኮ ሌላ ሌላውን እንጂ ምርጫውን ልማታዊ ሲል ሰምቼው አላውቅም (አሁን ይጀምር ይሆናል!) አንዱ ጐልማሳ መራጭ ደግሞ አስተያየታቸውን የጀመሩት የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር መለስን በማወደስ ነው፡፡ “የባለራዕዩን መሪ አርአያ ተከትለን…” አሉና እሳቸውም “ይሆነኛል…ይጠቅመኛል” ያሉትን መምረጣቸውን ነገሩን፡፡

አንደኛዋ ወይዘሮ ደግሞ ምን ብትል ጥሩ ነው? “ጫንቃችንን ያቃለለልንን ፓርቲ መርጫለሁ” (ኢህአዴግ ብላ ብትገላገልስ?) ከሁሉም ግን የኢራፓ ሊቀመንበር የሰጡትን አስተያየት የሚያህል የለም (ዊርድ እኮ ነው!) “ዝናብ የለም፤ ደመና ነው፤ ሙቀት የለም…ሁሉ ነገር ኖርማል ነው” (ስለምርጫ እንጂ ስለሜትሮሎጂ ማን ጠየቃቸው?) የሆኖ ሆኖ እስካሁን “የምርጫው ሂደት ዲሞክራሲያዊ፣ ፍትሃዊና ልማታዊ ነው” ተብሏል፡፡ ግን እኮ ድሮም ቢሆን በጥባጩ ህዝብ ሳይሆን ፓርቲዎቹ ናቸው - ገዢው ፓርቲና ተቃዋሚዎቹ! የብጥብጣቸውን ሰበብም አሳምረን እናውቀዋለን - የፈረደበት ሥልጣን ነው!! አሁን ግን የምርጫው ውጤት ቀድሞ የሚታወቅ ስለሆነ (መጨረሻው እንደሚታወቅ ፊልም) ፓርቲዎቹ አልተወዛገቡም (የተሳተፉት ማለቴ ነው!) ለነገሩ ብዙዎቹ ገና የኢህአዴግን ሚሊዮን እጩዎች ሲሰሙ እኮ ነው እጅ የሰጡት (የቤት ሥራቸውን አልሰሩማ!) እነዚህ የጦቢያ ተቃዋሚዎች ግን ሁነኛ መካሪ ሳያስፈልጋቸው አይቀርም (ቢቻል በዲሞክራሲ የዳበረ ልምድ ካላቸው አገራት!) እንዴ…”በምርጫ አንሳተፍም!”፣ “ፓርላማ አንገባም!”፣ “አንደራደርም” ምናምን እየተባለ እስከመቼ ይዘለቃል? እኔ የምጠረጥረው ምን መሰላችሁ? ወይ የፖለቲካ ጨዋታውን አላወቁበትም ወይ ደግሞ ኢህአዴግ አንድ ነገር አስነክቷቸዋል (የምህዳሩ መጥበብ እንዳለ ሆኖ ማለቴ ነው!) እንዴ ቢጠብም እኮ ባለችው ዕድል መንፈራገጥ ነው፡፡ ሽሽትማ ለማን በጀ? እንግዲህ ፖለቲካዊ ወጋችንን በእንካስላንቲያ እንደጀመርነው በእንካስላንቲያ እንቋጨው፡፡ (ለደራሲ ኃይለመለኮት መዋዕል ምስጋናችን ይድረሰው እያልን!) እንካስላንቲያ? በምንቲያ? በቁርቁስ! ምናለህ በቁርቁስ? አንጠርጥረህ ምረጥ ጥሩን ከልክስክስ ለምክር ቤት ምርጫ ዋሾን አታግበስብስ፡፡ (ወንዳታ ብለናል!!)