Administrator

Administrator

ዩኒቨርሳል ክሊኒክ የታይፎይድ በሽታን መርምሮ ውጤቱን በ37 ደቂቃዎች ውስጥ ለማረጋገጥ የሚያስችል መሣሪያ ማስመጣቱን የገለፀ ሲሆን፤ በታይፎይድ ህክምና ላይ በመላ አገሪቱ ይታዩ የነበሩ ችግሮችን ለመፍታት የሚያስችል መሆኑን የክሊኒኩ ሃኪም ተናግረዋል፡፡ በአገራችን ውስጥ በስፋት ሲያገለግሉ የቆዩ መሳሪያዎች ሁለት ጉድለት እንደነበረባቸው ዶ/ር ምክሩ ጠቅሰው፤ ምርመራው ፈጣንና አስተማማኝ አልነበረም ይላሉ፡፡ የታይፎይድ ባክቴሪያ በሰውነት ውስጥ እንዳለና እንደሌለ በፍጥነት ለማረጋገጥ የሚደረገው ምርመራ አስተማማኝ ስላልነበረ የተሳሳተ ውጤት ያመላክት ነበር ብለዋል፡፡

“ቀድሞ የነበረው መሣሪያ በሽታው ሣይኖር አለ ብሎ የሚያመላክትበት አጋጣሚ ስለነበር፤ ህመምተኛው ተገቢውን የህክምናና የመድሃኒት አገልግሎት በተገቢው መንገድ ጥርት ያለ ምርመራ ለማድረግም “Blood Culture” በሚባል የምርመራ ዓይነት ናሙናዎች ተወስደው ውጤቱን ከሣምንት በላይ መጠበቅ ግድ ነበር የሚሉት ዶ/ር ምክሩ፣ በሽተኛው እስከዚያ ድረስ ጉዳት ይደርስበታል ብለዋል፡፡ ክሊኒኩ አዲስ ያስመጣው መሣሪያ ትክክለኛውን የህክምና ውጤት በደቂቃዎች ውስጥ ከማሣወቁም በላይ በምርመራው ሂደት ይፈጠሩ የነበሩ ስህተቶችን ሙሉ ለሙሉ የማስወገድ አስተማማኝ መሳሪያ ነው ብለዋል - ዶ/ር ምክሩ፡፡

የሶርያ ምግቦች አዘጋጅቶ ለተጠቃሚዎች የሚያቀርብ ሬስቶራንት በ2 ሚሊዮን ብር ተቋቁሞ በአዲስ አበባ አገልግሎት መስጠት የጀመረ ሲሆን ሦስት ተጨማሪ ሬስቶራንቶችን ለመክፈት እንደተዘጋጀ ሶሪያዊው ባለሀብት ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያን ጨምሮ በግብጽ፣ ፊሊፒንስ፣ ዱባይ፣ ቤሩት እንዲሁም በሶሪያ ተመሣሣይ ሬስቶራንቶችን መክፈታቸውን የሚናገሩት የድርጅቱ ባለቤት አህመድ አሊ በክሪ፣ ሬስቶራንቱ የሶሪያ ባህላዊ ጣፋጭ መብሎችንም ሰርቶ በማቅረብ የሚያስተዋውቅ ነው ብለዋል፡፡

በሶሪያ ለምግብ የሚጠቀሙባቸው ግብአቶች ከኢትዮጵያ ጋር ተመሣሣይ እንደሆኑ ጠቁመው፤ ኢትዮጵያውያን የሶርያ ምግቦችን እንደሚወዷቸው እርግጠኛ ነኝ ብለዋል፡፡ “ሲሪያን ስዊት ኤንድ ሬስቶራንት” በተጨማሪ በአዲስ አበባ ለሚከፈቱ ሦስት ተመሣሣይ ሬስቶራንቶች ሠራተኞችን እያዘጋጀ ሲሆን፤ እስካሁን ለ12 ኢትዮጵያውያን ሼፎች የጣፋጭ ምግቦች አሠራር ስልጠና መሠጠቱን አህመድ በክረ ገልፀዋል፡፡ ከሬስቶራንት አገልግሎቱ በተጨማሪም በትላልቅ አለማቀፍ ስብሠባዎች የምግብ መስተንግዶ እንደሚያቀርቡ የተናገሩት ባለሀብት፣ አንድ የምግብ ኢንዱስትሪ ኩባንያን ለመግዛት በድርድር ላይ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡

ዱሮ የሠራሃቸውን ዘፈኖች እንደገና ተቀርጸሐል፤ ከአሁኑና ቀደም ሲል ከነበረው አሠራር እና ቴክኖሎጂ የትኛው ተሻለህ?

ከሃያ አራት ዓመታት በፊት የነበረው ጊዜ ስህተት ላለመሥራት የምንጠነቀቅበት በጣም ከፍተኛ የኾነ ትግልና ልፋት የሚጠይቅ፣ ጊዜ ነበር፡፡ እኔ በተለይ የመጀመሪያውን አልበሜን ላወጣ ሥራዬን ከሮሃ ባንድ ጋር ሠርቼ ካጠናቀቅኹ በኋላ ባንዱ ሁለት ዘፈኖችን እንዲያስተካክል አሣታሚው ሲጠይቃቸው ሥራ ስለሚበዛባቸው ይሁን መሥራት ባለመፈለጋቸው ፍቃደኛ ሳይኾኑ ቀሩ፡፡

ዘፈኖቹን ናሙናው ላይ እንደነበሩት አድርጌ አለመምራቴን አሣታሚው ስላመነበት ሌላ ስቱዲዮ ገብተን ሁለቱን ዘፈኖችና ሁሉንም አፍርሰን በአንድ ዓይነት አሠራር ለመቅረጽ ተስማምተን እንደገና ሠራናቸው፡፡ ሙዚቃውን የሠሩት ፈለቀ ኃይሉ፣ኃይለእግዚአብሔር ገዳሙና ነፍሱን ይማረውና ደረጀ ተፈራ ነበሩ፡፡ የቀረጸው ደግሞ እሱንም ነፍሱን ይማረውና አሣታሚው የ‹‹ሶል ኩኩ›› ባለቤት ሣህለ ነበር፡፡ ሙዚቀኞቹ ከሮሃ ባንድ የወጡ ስለነበሩ ‹‹አሞራ ባንድ›› የሚል አዲስ ስም አውጥተው አብረን ጥሩ ነገር ሠራን፡፡ ለእኔ ግን በጣም ፈታኝ እና አድካሚ ነበር ፡፡

ጨረስኩ ብዬ ሳስብ ከአንድ ባንድ ወደ ሌላ ባንድ ተሸጋግሬ መሥራቴ በጣም ልፋት ነበረው፡፡ ቴክኖሎጂውን በሚመለከት የመጀመሪያውን አልበሜን ዘፈን ለመቅረጽ ስንሰባሰብ ሰባራ ባቡር ይባል በነበረው ሰፈር ውስጥ አነስተኛ ሙዚቃ ቤት እና ከጀርባው ደግሞ ትንሽዬ ስቱዲዮ የመሰለ ቤት የነበረው ተክሌ ተስፋዝጊ ጋር ነበር የምንሠራው፡፡ ቤቷ በጣም ጠባብ ስለነበረች ሁላችንም በቅርበት ተጠጋግተን ዙሪያ ሠርተን ነበር የምንቀርጸው፡፡ ሁለተኛውንም አልበም ስሠራም ከ‹‹ሶል ኩኩ›› ሙዚቃ ቤት ጋራ በጋራ ይሠራ የነበረው የ‹‹ናዲ›› ሙዚቃ ቤት ባለቤት የእነኑረዲን መኖሪያ ቤት እንቁላል ፋብሪካ አካባቢ ይገኝ ነበር፡፡ ሳሎን ቤታቸው ሰፋ ያለ ስለነበር እዛ ነበር የቀረጽነው፡፡ ዘፈኑ የሚቀዳው ደግሞ በዴክ ስለነበር ሁሉም ነገር የሚቀረጸው አንድ ላይ ነበር፡፡

ቀረጻው ከተበላሸ ከመጀመሪያው ጀምሮ እንደገና ይቀዳል፡፡ ዛሬ ግን እኔ ባበላሽ የሚደገመው የእኔ ብቻ ነው ያውም ያበላሸኋት ቦታ ተለይታ፡፡ አንዱ ሙዚቀኛ ቢበላሽበትም እንደዚያው ለብቻው ገብቶ ይሠራዋል፡፡ የአሁኑ አደረጃጀቱም ኾነ የድምጽ መቅረጫ መሳሪያዎቹ ዘመናዊነት የሚያጠያይቅ አይደለም ከዚህ አንጻር ሳየው የቀድሞው የእኛ ልፋት ተወዳዳሪ አይገኝለትም፡፡ ለድምጻዊው ግን በጣም ጠቃሚ የኾነ አሠራር ነበር፡፡ ለዘፈኖቹ ከፍተኛ ግምት በመስጠት በተደጋጋሚ ጥናት የዳበረ ሥራ ስለሚኾን ወደ ሰው ጆሮ ሲደርስ የሚደመጥ ያደርገዋል፡፡ መድረክ ላይ ሲወጣም የተዋጣለት ሥራ ለመሥራት ያስችላል፡፡

ዛሬ ለሥራው ግምት አይሰጥም ማለቴ ሳይኾን ያለምንም ጥናት በአንድ ቀን ሁሉንም ነገር የሚጠናቀቅበት አሠራር አለ፡፡ ከዚህ አንጻር የዛን ጊዜውን ያህል የጠነከረ ሥራ ይሠራል ማለት ይከብዳል፡፡

ዘፈኖቹን የተቀረጽከው እንደ አዲስ በመኾኑ ልፋቱ እንዴት ነበር?

ዘፈኑን የሚያውቁትን ባለሞያዎች አሰባስቤ በክብረት መሪነት የተሠራ ነው፡፡ ዘፈኖቹን በጥሩ ሁኔታ ያደራጃቸው እና በሙዚቃው ሕግ መሠረት መስመር ያስያዘው ደግሞ ፈለቀ ነው፡፡ እኔ ድምጼን የሰጠሁት ፈለቀ አስተካክሎ ባመጣው ሙዚቃ ነው፡፡ ከዛ በኋላ ሙዚቀኞቹ ገብተው ሠሩት፡፡ በዚህም ምክንያት ምንም የሥራ ጫና ሳይኖርብኝ በተረጋጋ ሁኔታ ነው የሠራነው፡፡ በዚህ በኩል ባለሞያዎቹ ትልቅ አስተዋፆ አላቸውና ላመሰግናቸው እፈልጋለሁ፡፡

ለምን እንደገና መሥራት ፈለክ?

ዘፈኖቼ በብዛት የነበሩትና አሁንም ያሉት በኦዲዮ ካሴት ላይ ነው፡፡ የዛን ዘመን ቴክኖሎጂ እየቀረና በአዳዲስ እየተተካ ሲመጣ ይህ ትውልድ ከእኔ ዘፈን ጋር እየተራራቀ ሊሄድ ይችላል የሚል ስጋት አደረብኝ፡፡ ዕድሜዬም ለዱላ ማስያዝ ከመድረሱ በፊት መዘጋጀት እና ለትውልዱ አንድ ነገር ትቼ ማለፍ አለብኝ በሚል አስቤ ነው እንደ አዲስ ስቱዲዮ ገብቼ ነው የሠራሁት፡፡ ዘፈኖቹን ከየአልበሞቹ ላይ እንዴት መረጥካቸው? ለሰው ጆሮ ቅርብ ናቸው ያልኳቸውን ዘፈኖች ነው የመረጥኩት፡፡ በዛን ዘመን ዘፈን ስናወጣ የአልበም ስያሜ አልነበረውም፡፡ አንዱን ዘፈን መርጠን ነው መጠሪያ የምናደርገው፡፡ ‹‹እሄዳለሁ ሐረር›› የሚለው ዘፈን ካለበት የመጀመሪያው አልበም ላይ ስድስት ዘፈን መረጥኩ፡፡ ‹‹ለሠርጓ ተጠራሁ›› ካለበት ሁለተኛው አልበም ደግሞ አራት ዘፈን መረጥኩ፡፡ ከሦስተኛው አንድ ዘፈን መረጥኩና ሌሎቹን ከተለያዩ ድምፃውያን ጋራ ከሠራኋቸው ኮሌክሽኖች በአጠቃላይ 14 ዘፈን ነው መርጬ በድጋሚ የሠራሁት፡፡ በምርጫዬም የተከፋ ሰው የለም፡፡

ከቀድሞው ጋራ የድምፅ ልዩነት የለውም?

ብዙ የተለየ ነገር የለውም፡፡ ምናልባት በጉርምስና ወቅት የተሠራና ዕድሜ 40ን ካለፋ በኋላ የሚሠራ ሥራ ትንሽ ልዩነት ያመጣል የሚል ሐሳብ ከተነሳ አሁን ያኔ ከነበረኝ ነገር ትንሽ በሰል ያልኩበት ሥራ ይመስለኛል፡፡ እንዲህ ያለውን ዘፈን ለምን አላካተትክም ያለህ የለም? እንደሱ የሚልማ በጣም በርካታ ሰው አለ፡፡ በአብዛኛው የሚወደውን ዘፈን እያስታወሰ ለምን እንዳስቀረሁት ይጠይቀኛል፡፡ በአንድ ጊዜ ሁሉኑም ዘፈን ማካተት ስለማይቻል የቀሩትን ዘፈኖች አሰባስቤ የማውጣት ሐሳብ እንዳለኝ እነግራቸዋለሁ፡፡ ነገር ግን አሁን ይፋ በማላደርገው መንገድ የምሠራው አንድ አልበም፣ አንድ አልበም ደግሞ በተለመደው ስልት የምሠራው እንዲሁም ከአብርሃም ወልዴ ጋራ አንድ ነጠላ ዜማ እስከነ ቪዲዮ ክሊፑ የመሥራት ዕቅድ ስላለኝ እነዚህን ስጨርስ በኦዲዮ ካሴት ያሉትን ሁሉንም ሥራዎቼን አሰባስቤ ወደ ሲዲ መቀየር እፈልጋለሁ፡፡

ከመጀመሪያው አልበምህና ከአሁኑ በወጪ ደረጃ የቱ ፈታኝ ነው?

የመጀመሪያውን አልበሜን ስሠራ ሁሉንም ወጪ የሸፈነው ሙዚቃ ቤቱ ነበር፡፡ እኔን ከፍሎ አዘፈነኝ እንጂ ለማን ምን ያህል ገንዘብ እንደከፈለ የማውቀው ነገር እንኳን አልነበረም፡፡በወቅቱ የማውቀው ነገር ቢኖር ለሮሃ ባንድ ተከፍሎት የነበረውን ዐስራ አንድ ሺሕ ብር ብቻ ነው፡፡ሆኖም የቱንም ያህል ቢከፍል አሁን እኔ ለዜማ፣ለግጥም እና ለቅንብሩን ካወጣሁት ወጪ ጋር የሚደራረስ አይሆንም፡፡ እኔም አሁን ማስተሩን ለናሆም ሪከርድስ የሸጥኩበት ዋጋ ያኔ ከተከፈለኝ ጋር በፍጹም የሚቀራረብ አይደለም፡፡

ለመጀመሪያው አልበም ሥራህ ሙዚቃ ቤት ያገናኘህ ኮመዲያን ልመንህ ነበር፡፡ ኮሚሽን ከፍለኸው ነበር?

ልመንህ ታደሰ እኔን ብቻ ሳይኾን ነፍሱን ይማረውና ኬኔዲ መንገሻንም ከሶል ኩኩ ሙዚቃ ቤት ጋራ ያገናኘው እርሱ ነበር፡፡ እኔ በዛን ጊዜ የተዋዋልኩት በሦስት ሺሕ ብር ነበር፡፡ ግማሹን መጀመሪያ ተቀብዬ ቀሪው መጨረሻ ላይ ነው የተከፈለኝ፡፡ በወቅቱ ደግሞ አብረን አንድ ኪነት እንሠራ ስለነበር እርሱም ስጠኝ አላለኝም እኔም ኮሚሽን አልከፈልኩትም፡፡ በዛን ጊዜ ደግሞ ኮሚሽን የሚባል ነገር አይታወቅም ነበር፡፡

ሐሳቡም ቢተነፈስ ክፍያ የሚጠየቅበት ዘመን ላይ የደረስነው አሁን ነው፡፡

ልመንህን አግኝተኸው ታውቃለህ?

አሜሪካ እያለ በብዛት አገኘው ነበር እዚህ ከመጣ በኋላ ግን አግኝቼው አላውቅም፡፡ ለማግኘት በጣም ሞክሬ ነበር ስልም አልዋሽም፡፡ አልበምህን ባወጣህ ሰሞን ወደ ድሬደዋ እና ሐረር ለ27 ቀናት ኮንሰርት ሠርተህ ነበር ክፍያው ጥሩ ነበር? ለሥራው የወሰዱኝ ጅጅጋ ውስጥ የነበሩ የወታደር ባንድ ነበር፡፡ በቀን 700 ብር ይከፈለኝ ነበር፡፡ መድረክ ላይ በወጣሁ ቁጥር ደግሞ ሽልማት ነበረኝ፡፡ የሄድኩት አልበሜ በወጣ በአንድ ወሩ ስለነበር በዚያች በአጭር ጊዜ ድሬደዋ፣ሐረር፣ጅጅጋ፣አለማያ፣ ሂርና እያዞሩኝ ስዘፍን ሕዝቡ ዘፈኖቼን ለምዶና ወዶት ስለተቀበለኝ ገንዘቡ ላይ ትኩረት አላደረኩበትም እንጂ የቆየሁበት ቀናት ተቆጥሮ ለወቅቱ በጣም ጥሩ ክፍያ ነበር የተከፈለኝ፡፡ በዛ ላይ ሁሉንም ወጪዬን ችለው እንዲሁም የምንጓጓዝበትን ትራንስፖርት ሸፍነው ስለሚያንቀሳቅሱኝ የሰጡኝን ገንዘብ ሳልነካው ነበር አዲስ አበባ የተመለስኩት፡፡

በምን ነበር የምትጓጓዙት?

ዘፋኝ ስለነበርኩ ጋቢና ይታዘዝልኛ እንጂ በ‹‹አይፋ›› (ትልቁ የወታደር መኪና) እየተጓጓዝን ነበር የምንሠራው፡፡

ምን ዓይነት መድረክ ላይ ነበር የምትሠራው? ምን ያህል ሰው ይታደም ነበር?

በተለያዩ አዳራሾች ውስጥ ነበር፡፡ እኛ ከመድረሳችን በፊት ከተማ ውስጥ እየገቡ የሚቀሰቅሱ ልጆች ስለነበሩ የከተማውን ሰው አነቃቅተው ይጠብቁናል፡፡ በአንድ መድረክ እስከ 400 ሰው ይታደም ነበር፡፡ በጣም ደስ የሚል ጊዜ ነበር፡፡

‹‹እሄዳለሁ ሐረር ባቡር ተሳፍሬ›› የሚለው ዘፈንህን የሚያዳምጡ ሰዎች ‹‹አንደኛ ሐረር ባቡር የለም፡፡ ሁለተኛ እርሱ የሚለውን ፍራፍሬ የለም›› ሲሉ ይወቅሱሃል፡፡ የቪዲዮ ክሊፑንስ እዛው ሄደህ ነበር የተቀረጽከው?

አይደለም፡፡ አዲስ አበባ ስቱዲዮ ውስጥ ነው የተቀነባበረው፡፡ ግን ቦታው ሂርና አካባቢ ነበር፡፡ ሐረር ከባቡር ጋራ ለምን ተያያዘ ለሚባለው መውረጃው ድሬደዋ ይሁን እንጂ ሐረር ለመሄድ እኮ ባቡር መሳፈራችን ግድ ነበር፡፡ከድሬደዋ በኋላ በመኪና ሐረር እንገባለን፡፡ ፍራፍሬውም በወቅቱ የነበረው ነው፡፡ ያን ግዜ ስንሄድ የነበረው ጫካ ውበት ራሱ ትዝ ይለኛል፡፡ እንደዛኛው ግዜ በብዛት አይኑር እንጂ በፍራፍሬ እንኳን ሐረር እና ድሬደዋ አሁንም አይታሙም፡፡ ሁለቱም በጣም የምወዳቸውና የሚመቹኝ ከተሞች ናቸው፡፡

የሠርግ ሥራዎችህን ቀጠሮ በመያዝና በመደራደር በአገር ፍቅር ትያትር ቤት የዘመናዊ ዳንስ አሰልጣኟ ባለቤትህ ወ/ሮ ዘነበች ጌታሁን እንደምታግዝህ ሰምቻለሁ፡፡ ከአንተ እና ከእርሷ ዋጋ ማን ይቀንሳል?

ባለቤቴ ሥራ ስላላት የምታግዘኝ በትርፍ ጌዜዋና ከኢትዮጵያ ውጭ ስሆን ነው እንጂ እኔ ሁልጊዜ እርሷ ብትሆንልኝ ደስ ይለኛል፡፡ ምክንያቱም እኔ ብዙ የማወዳድራቸው ነገሮች አሉ አንዳንድ ግዜ እኔ ተጎድቼ ብሠራስ የምልባቸው ሥራዎች አሉኝ፡፡

ሴቶች ሰዎችን አግባብቶ የማሠራት አቅም ስላላቸው ለንግድ ሥራ ጎበዝ ናቸው፡፡ ስለዚህ እርሷ ስትሆን ጠንከር ስለምትል ጥሩ የመደራደር አቅም አላት፡፡

አልበም ከማውጣትህ ካለፉት 25 ዓመታት ጀምሮ በዓመት ከ30 እስከ 40 ሠርግ ትሠራለህ?

በተለየ ሁኔታ የምታስታውሰው ሠርግ እና ሙሽራ አለ? ማስተካከያ ይደረግልኝ፡፡ የተጠቀሰው ቁጥር ቀደም ሲል የነበረ ነው፡፡ ካለፉት ሁለት እና ሦስት ዓመታት ወዲህ የሠርግ ሥራ ቀንሷል በዓመት 15 ሠርግ እንኳን አይገኝም፡፡ ለዚህ ደግሞ ጊዜ ያመጣቸው የተለያዩ ምክንያቶቹ አሉ፡፡ በእኔ በኩል ግን ይችን ታህል ካገኘን ተመስገን ይበቃል ነው የምለው፡፡ የሚገርመው ከዚህ ሁሉ ሙሽራ ላወራበት የምችለው በተለየ የማስታውሰው የተጋነነ ነገር የለኝም፡፡

የሠርግ ሥራ መለያህ ኾኗል፤ ኮንሰርት ትሠራለህ?

አዎ ከኢትዮጵያ ውጪ እየተጋበዝኩ ለተለያዩ ፕሮግራሞች እሠራለሁ፡፡ እዚህ አገር ግን ፕሮግራም ይኖረዋል ወይም ደግሞ ጸጋዬ የሠርግ ድምፃዊ ብቻ ነው ተብሎ እንደሆነ አላውቅም ኢትዮጵያ ውስጥ ብዙ አልታይም፡፡ ምናልባት ነገ ከነገወዲያ ምን እንደሚፈጠር አላውቅም፡፡      የማኅበራዊ ድረ-ገጽ ፌስቡክ ተጠቃሚ ነህ?

አዎን ተጠቃሚ ነኝ፡፡ ፌስቡክ በጣም ጠቃሚ ነገር መሆኑን ያወኩት አሁን ነው፡፡ ዱሮ አልበም ስናወጣ የሕዝቡን አስተያየት ማግኘት የምንችልበት መንገድ በጣም የተጣበበ ነበር፡፡ ግፋ ቢል አንዳንድ ታታሪ ሰዎች በፖስታ ከሚልኩት አስተያየት በቀር እንዲህ በቀጥታ አስተያየት የምናገኝበት እኛም የምንፈልገውን መልእክት በፈለግነው ሰዓት በቀጥታ የምናስተላልፍበት መንገድ አልነበረም፡፡ አሁን ይህንን አዲሱን ሥራዬን ስሠራ ሥራዬን አስተዋውቄበታለሁ፡፡ ወዳጆቼም ከሚገባው በላይ አስተያየት በመስጠት አበረታተውኛል፡፡ ይህ ደግሞ በጣም አስደስቶኛል፡፡ በቅርቡ የተቋቋመው የድምፃውያን ማኅበር ፕሬዝዳንት ነህ ከምስረታችሁ በኋላ ምን ሠራችሁ? ማኅበሩን የመሰረትነው በቅርብ ነው፡፡ ለረጅም ጊዜያት ለድምፃውያን የሚናገሩላቸው ሌሎች ሰዎች ነበሩ፡፡

ነገር ግን የራሳቸው የኾነ በርካታ ችግሮች አሏቸው፡ ይህን ችግራችንን ሰብሰብ ብለን በጋራ ለምን አንፈታውም በሚል የሞያ ማኅበር መቋቋሙን አምነንበት ነው የመሠረትነው፡፡ የማኅበሩን ፈቃድ ካገኘን በኋላም በርካታ ድምፃውያንን በአባልነት ተቀብለን ደስ በሚል መንፈስ የመጀመሪያ ጠቅላላ ጉባኤያችንን አካሂደን ጉባኤው አመራሩን መርጧል፡፡ ለቦርድ አመራርነት የተመረጥነው እኔን ጨምሮ አመልማል አባተ፣ ሚካኤል በላይነህ፣ ቴዎድሮስ ሞሲሳ፣ ጸደኒያ ገ/ማርቆስ፣ ታደለ ገመቹ እና ብርሃኑ ተዘራ ነን፡፡ አሁን ብሬ ላልተወሰነ ጊዜ ከኢትዮጵያ ውጪ ስለምሄድ በሌላ ሰው ተኩኝ እያለ ነው፡፡ እናም አሁን ማኅበሩን በገንዘብ ለማጠናከር የሚያስችለንን ሥራ እየሠራን ነው፡፡ በቀጣይ ባለን ዕቅድ ለባለሞያው ጠቃሚ የኾነ ጥሩ ሥራዎችን ለማከናወን እየተንቀሳቀስን ነው፡፡ ይህን ደግሞ ወደፊት የምታዩት ይኾናል፡፡

“መንግስት ለትውልድ የሚተርፍ የማያልቅ እዳ ውስጥ እየገባ ነው” መንግሥት የሱቅ ነጋዴ ቢሆን በአንድ ሳምንት ሱቁን ይዘጋ ነበር ትልቁ ሙያ ግሽበቱን ቀንሶ፣ ብሄራዊ ምርቱን አሳድጐ፣ ስራ አጥነትን መቀነስ ነው የዋጋ ግሽበቱ የቱ ጋ ነው የወረደው ---- ስኳር ላይ ነው? ዘይት ላይ ነው? ጤፍ ላይ? ኢህአዴግ በቅርቡ ባህርዳር ላይ ባካሄደው ድርጅታዊ ጉባኤው አጠቃላይ የአገሪቱ ኢኮኖሚ መቀዛቀዝ እንዳሳሰበው ገልጿል፡፡ በሌላ በኩል የዋጋ ግሽበት በከፍተኛ ደረጃ እየቀነሰ መምጣቱን ከማዕከላዊ ስታትስቲክስ ቢሮ የወጡ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ አንዳንድ የኢኮኖሚ ባለሙያዎች እንደሚሉት ኢህአዴግ ቀደም ሲል የተሰጡትን ሙያዊ ምክሮች አለመስማቱ አሁን በኢኮኖሚው ማሽቆልቆል ዋጋ እያስከፈለው ነው፡፡ በ97 ምርጫ ቅንጅትን ወክለው በመወዳደር ፓርላማ የገቡትና በኢኮኖሚ ጉዳዮች ላይ ከአገሪቱ የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ጋር ክርክርና ሙግት በመግጠም የሚታወቁት አቶ ተመስገን ዘውዴ፤ በአሁኑ ሰዓት መንግሥት ቀንሷል የሚለው የዋጋ ግሽበትም እንደተባለው አለመቀነሱን ይናገራሉ፡፡

ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ የአንድነት ፓርቲ የውጭ ጉዳይ ሰብሳቢና የመድረክ ስራ አስፈፃሚ አባል የሆኑትን አቶ ተመስገን ዘውዴን በአገሪቱ ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ዙሪያ አነጋግሯቸዋል፡፡ ከፓርላማ ከወጡ በኋላ ለምን ከሚዲያው ጠፉ? ወድጄ አይደለም፡፡ አብዛኛው ሚዲያ በገዢው ፓርቲ ቁጥጥር ስር ነው ያለው፡፡ ይኼ ደግሞ ሃቁን የሚናገሩ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የሚናገሩት ነገር ለገዢው ፓርቲ ሊዋጥለት ስለማይችል ነገሩን አድበስብሰው ከሚያልፉት ጋር ብቻ ከማቀንቀን ብዬ ነው የጠፋሁት፡፡ የሚዲያ አማራጭ የለንም፡፡ አሉ የሚባሉትን ነፃና ገለልተኛ የፕሬስ ውጤቶች ገዢው ፓርቲ እንዳይታተሙ በማድረጉ ብዙም የሚዲያ እድል ስለሌለኝ ነው እንጂ የምናገረው ነገር በማጣት አይደለም፡፡ አሁን ምን እየሠሩ ነው? ከፓርላማው ከወጣሁ በኋላ በፓርቲዬ “አንድነት” ውስጥ እያገለገልኩ ነው፡፡ የፓርቲው የውጭ ግንኙነት ጉዳይ ኃላፊ ሆኜም እየሰራሁ ነው፡፡

አሁን ያለው ፓርላማ እርሶ ከነበሩበት ፓርላማ አንፃር በሀገሪቱ ወሳኝ ጉዳዮች ላይ የሚያደርጋቸውን ውይይቶችና የሚያስተላልፋቸውን ውሳኔዎች እንዴት ይገመግሙታል? እኔ በነበርኩበት ፓርላማ ይብዛም ይነስም 172 የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ነበሩ፡፡ እነዚህ አባላት በሙሉ አቋማቸው ግልፅ ነበር፡፡ እዚያ ውስጥ ያለነው የፓርላማ አባላት በተለይ እኔ የነበርኩበት የመጀመሪያው ቅንጅት፣ ቀጥሎም አንድነት የህዝብን አንገብጋቢ ጥያቄዎችና የመንግሥትን ፖሊሲ የመሳሰሉትን አንስተን ወደ ፓርላማው ለማቅረብ ባንችልም በነዚህ ዙሪያ የሚነሱ ሃሳቦችን በቀጥታ በመጋፈጥ ለህዝብ ይጠቅማሉ ያልናቸውን ሃሳቦች በትክክል ህዝቡ እንዲሰማ አድርገን እናቀርብ ነበር፡፡ አሁን ግን ገዢው ፓርቲ ሙሉ ለሙሉ ፓርላማውን ስለተቆጣጠረ የሚወጡት አዋጆች የኢትዮጵያን ህዝብ ሰላም፣ ዲሞክራሲያዊ ነፃነት እና የሰብአዊ መብት ጥበቃ ወደ ኋላ የሚጐትቱ መሆናቸውን ለማሰማት የሚደረጉ ጥረቶች ደካማ ናቸው፡፡

ይሄም ከገዢው ፓርቲ ተፅእኖ የሚመጣ ነው ለማለት እችላለሁ፡፡ ባለፈው ግን ቁጥራችንም ብዙ ስለነበረ በምትሰጠን ጥቂት ደቂቃ ውስጥ ከፍተኛ የህዝብ ስሜትን ሊይዝ የሚችል ክርክር በፓርላማው ውስጥ በማድረግ ለህዝቡ ያለንን ታማኝነትና ቆራጥነት ለማሳየት የቻልንበት ሁኔታ ነበር፡፡ አጠቃላይ የሀገሪቱ ኢኮኖሚ እየተቀዛቀዘ መሆኑን መንግሥትም አለማቀፍ ተቋማትም ገልፀዋል፡፡ ምክንያቱ ምን ይሆን? እንግዲህ እዚህ ሀገር አንድ ገዢ ፓርቲ ከማዕከል እስከ ቀበሌ ፍፁም በሆነ አስተዳደራዊ የበላይነት እያስተዳደረ ነው፡፡ ኢኮኖሚው በሁለት አሃዝ ጨምሯል ሲባል በእርግጥ ጨምሯል ወይ ብለን ከሦስተኛ ወገን የምናጣራበት መንገድ የለም፡፡ ኢኮኖሚው ላለፉት ሦስትና አራት አመታት እያደገ ነው ሲባል እየሰማን ነው፡፡ የኢኮኖሚ እድገት ዞሮ ዞሮ ተጠቃሚ ማድረግ ያለበት ህብረተሰቡን ነው፡፡ መሠረታዊ የሆኑ ነገሮችን እንደ ምግብ፣ መጠለያና አልባሳትን ማሟላት አለበት፡፡ የኢኮኖሚ እድገቱም በዚህ ነው የሚታየው፡፡ ገዢው ፓርቲ ኢኮኖሚው በሁለት አሃዝ አድጓል ሲል እኛ አልተቀበልንም፡፡ ብሄራዊ ምርት (GDP) ከዓመት ዓመት አድጐ እንኳ ቢሆን ኖሮ የማክሮ ኢኮኖሚ አስተዳደር የሚጠይቀው ብሄራዊ ምርቱን ማሳደግና የዋጋ ግሽበቱን መቆጣጠር ነው፡፡

በማክሮ ኢኮኖሚ አስተዳደር ሙያ፤ ብሄራዊ ምርት (GDP) ማሳደግ ብቻ አይደለም ትልቁ ነገር፣ ኢኮኖሚውን እያሳደጉ የዋጋ ግሽበትን መቆጣጠር ነው፡፡ ትልቁ ነገር ስራ አጥነትን መቀነስ መቻል ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ ግን እያየው ያለው ከፖለቲካዊ አንድምታው አንፃር ብቻ ነው፡፡ ብሔራዊ ምርቱ በማደጉ ምክንያት ዜጐች በገቢያቸው ለመተዳደር አለመቻላቸውን እንደ ቁምነገር አይቆጥረውም፡፡ ግን ትልቁ ቁምነገር እሱ ነው፡፡ የዋጋ ግሽበትን መቆጣጠር ሳይቻል ብሄራዊ ምርት አድጓል ማለት በቀኝ ሰጥቶ በግራ እጅ መቀበል ነው፡፡ ምክንያቱም ዜጐች በዋጋ ግሽበት ምክንያት በገቢያቸው መተዳደር ካልቻሉ የብሄራዊ ምርት ማደጉ ትርጉም የለውም፡፡ በማክሮ ኢኮኖሚ አስተዳደር ሙያ፤ ብሄራዊ ምርት አድጓል ማለት መንግሥት ወጪውን ሳይቀንስ ብር እያፈሰሰ ነው ማለት ነው፡፡ ትልቁ ሙያ ያለው ግሽበቱን ቀንሶ፣ ብሄራዊ ምርቱን አሳድጐ ስራ አጥነትን መቀነስ መቻሉ ላይ ነው፡፡ ብሄራዊ ምርቱ በማደጉ ምክንያት ዜጐች ተጠቃሚ ሆነዋል ወይ የሚለው ያልተመለሰ ጥያቄ ነው፡፡

በምሳሌ ላስረዳ፤ የዛሬ አራት ዓመት አምስት ብር በኪሎ የሚሸጥ ሙዝ ዛሬ 12 ብር ነው፣ በተቃራኒው የዛሬ አራት ዓመት 3ሺህ ብር በወር የሚያገኝ የመንግሥት ተቀጣሪ ዛሬም 3ሺህ ብር እያገኘ ነው፡፡ ታዲያ ይኼ ዜጋ እንዴት ነው ከእድገቱ ተጠቃሚ የሆነው፡፡ የብር የመግዛት አቅሙ መሬት ወድቋል፡፡ መንግሥት ግን ብሄራዊ ምርቱ አደገ እያለ ነው፡፡ ምን ጥቅም አለው ይሄን ማለቱ? ዜጐች በገቢያቸው መተዳደር ካልቻሉ፣ ሸማቹ ህብረተሰብ በገቢው መተዳደር ካልቻለ ዋጋ የለውም እያልን ነው፡፡ አሁን የዋጋ ግሽበቱ ወረደ እያሉን ነው፡፡ የቱ ጋ ነው የወረደው? እንደ ኢትዮጵያዊ የምንመገባቸውን ምግቦች እናውቃቸዋለን፡፡ የሰብል ምግቦች ዋጋ ላይ ነው የተሻሻለው? ስኳር ላይ ነው? ዘይት ላይ ነው? ጤፍ ላይ ነው? እስቲ የቱ ላይ ነው የወረደው፡፡ ይኼንን በተገቢው መንገድ ማስረዳት አለባቸው፡፡ የዋጋ ግሽበቱ በአይ ኤም ኤፍ የሐምሌ 2004 ዓ.ም መረጃ መሰረት፤ 33 በመቶ ደርሷል ይላል፡፡

አሁን ደግሞ እነሱ ወደ 12.9 በመቶ ዝቅ ብሏል እያሉን ነው፡፡ በጣም የሚገርም ሂደት ነው፤ የዋጋ ግሽበት ወደ ላይ ለመውጣትም ጊዜ ወስዶ ነው የሚወጣው፡፡ አወጣጡም አወራረዱም የራሱ መንገድ ስላለው የዋጋ ግሽበቱ በአራት እና አምስት ወር ጊዜ ውስጥ ከ33 በመቶ ወደ 12.9 በመቶ ወረደ ማለት መቶ ኪሎ ሜትር በሰዓት እየበረረ የሚሄድ መኪና ከመቅፅበት ቆመ እንደማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ሌላ የሚያስከተለው ጉዳት አለ፡፡ ወረደ ከተባለ በምን ምክንያት ነው የወረደው? የወጣውስ በምን ምክንያት ነው? የሚለው ተተንትኖ ሊቀርብ ይገባዋል፡፡ ይህ ባልሆነበት ሁኔታ ንግግራቸው የሃቅ ነው ማለት አይቻልም፡፡ ለፖለቲካ ፍጆታ የሚነገር ብቻ ይሆናል፡፡ ዛሬ አብዛኛው የኢትዮጵያ ህዝብ በገቢው መተዳደር፣ ልጆቹን ማስተማር፣ የቤት ወጪውን መሸፈን ባልቻለበት ሁኔታ እንዲህ አይነት የፕሮፓጋንዳ ምላሾች አስገራሚ ናቸው፡፡ ገዢው ፓርቲ የመንገድ መሰራትና የህንፃዎች መብዛትን ከፍተኛ የልማት ስኬት አድርጐ ነው የሚወስደው፡፡ ሃቁ ግን ይህ አይደለም፡፡

አስቀድሜ እንዳልኩት የህዝቦች የኑሮ ደረጃ የሚለካው በብሄራዊ ምርት (GPD) እድገት ብቻ አይደለም፡፡ የተባበሩት መንግሥታት ሂውማን ዴቨሎፕመንት ኢንዴክስ (የሰብዓዊ ልማት መለኪያ) የሚል ሪፖርት አውጥቷል፡፡ በዚያ መለኪያ መሰረት ኢትዮጵያ ከ178 ሀገሮች 174ኛ ደረጃ ነው የተሰጣት፡፡ የመጨረሻውን ረድፍ ነው የያዘችው፡፡ ይኼ ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ እስከ 12 ሚሊዮን የሚደርስ ህዝብ የምግብ ሰቆቃ ያለበት ሀገር ኢኮኖሚው አድጓል ቢባል ትርጉም የሚሰጥ አይደለም፡፡ አሁን ግን እድገቱ ቀንሷል እያለ ነው መንግሥት፡፡ ይኼ ምንን ነው የሚያመለክተው? እንግዲህ ትክክለኛውን እንናገር ከተባለ የዋጋ ግሽበት የሚባለውን ኢህአዴግ አልፈጠረውም፡፡ በማንኛውም ኢኮኖሚ ውስጥ የሚያጋጥም ጉዳይ ነው፡፡ የተለያዩ የኢኮኖሚ “ሳይክሎች” አሉ፡፡ ግሽበት ውስጥ የምንገባው፣ ኢኮኖሚው ሊሸከመው ከሚችለው በላይ ገንዘብ እየታተመ ወደ ኢኮኖሚው ሲገባ ነው፡፡ በመሰረቱ ግሽበት ማለት “ጥቂት ምርትን ብዙ ገንዘብ ሲያሳድድ” ማለት ነው፤ ሌላ ትርጉም የለውም፡፡ አሁን ምርቱ የለም፤ ብዙ ገንዘብ አለ ማለት ነው፡፡ ለዚህ ነው አንድ ዶላር 20 ብር ድረስ እየተመነዘረ ያለው፡፡

እንደዚህ ያሉ የግሽበት ሂደቶች ውስጥ ሲገባ ኃላፊነት የሚሰማው ገዢ ፓርቲ ሊወስዳቸው የሚገቡት እርምጃዎች አሉ፡፡ አንደኛው የመንግሥት ወጪን መቀነስ ነው፡፡ የመንግስት ወጪ እንዲቀንስ የሚደረግበት ምክንያት አለው፣ ኢኮኖሚው መሸከም ከሚችለው በላይ የብር ፍሰት ካለ መንግሥት ወጪውን መቀነስ አለበት፡፡ ይሄን ሌሎች ሀገራት እያደረጉ ያሉት ሞኝ ስለሆኑ አይደለም፤ “ኮንቬንሽናል የማክሮ አስተዳደር” የግዴታ ይሄን ስለሚጠይቅ ነው፡፡ ሌላው የበጀት ጉድለት እንዲጠብ መደረግ አለበት፡፡ እዚህ ግን የበጀት ጉድለቱ እንዲሰፋ እየተደረገ ነው፡፡ ሌላው ዜጐች ከባንክ የሚያገኙት የወለድ መጠንና የባንኮች ተቀማጭ ገንዘብ ከፍ እንዲል ይደረጋል፡፡ ምክንያቱም ገንዘብ ከኢኮኖሚው ውስጥ ለመሰብሰብ ይጠቅማል፡፡ ሌሎችም ብዙ መንገዶችም አሉ፤ መንግሥት ይሄን ለማድረግ አይፈልግም፡፡ ከዚህ አንፃር አሁን እድገቱ ቀነሰ ሲባል ምን ሆኖ ቀነሰ የሚለውን እናነሳለን፡፡ የመንግሥት ወጪ ቀንሶ አይደለም እንዲያውም እየጨመረ ነው ያለው፡፡ የበጀት ጉድለቱ እየጠበበ ነው? አይደለም እንደውም እየሰፋ ነው፡፡ የወለድ መጠኑም እየጨመረ አይደለም፣ ብሄራዊ ባንክም ገንዘብ እያተመ ወደ ገበያው ማሰራጨት አቁሟል ማለትም አይደለም፡፡

ስለዚህ በየትኛውም መንገድ ሚዛን ላይ ሊቀመጥ የሚችል ገለፃ የሌለው ነው፡፡ አሁን ብሄራዊ ምርቱ (GDP) ወርዷል ነው ያሉት፡፡ ቢወርድም እኛ እያየን እንዳለነው የዋጋ ግሽበቱ እየቀነሰ አይደለም፣ የስራ አጥ ቁጥር እየቀነሰ አይደለም፡፡ በተመሳሳይ ኢኮኖሚው ከፍተኛ መቀዛቀዝ ውስጥ ገብቷል እያሉን ነው፡፡ ከ11.5 ወደ 8.5 በመቶ በአራትና በአምስት ወር ጊዜ ውስጥ መውረድ ከፍተኛ ለውጥ ነው፡፡ ኢኮኖሚው የሚመራው በፖለቲካው ስለሆነ የትኛውንም ዓይነት መረጃ ለመቀበል ያስቸግረናል፡፡ ያኔም የሚናገሩት ችግሮችና መፍትሄዎቹ የተዛቡ ናቸው፤ አሁንም የሚናገሩትና መፍትሄ የሚሉት ነገር የላቸውም፡፡ ስለዚህ ኢኮኖሚውን በሙያ፣ በግንዛቤ መተንተን ሳይሆን ለፖለቲካ ፍጆታ ብቻ መጠቀም ነው የያዙት፡፡ የኢኮኖሚው መቀዛቀዝ ምናልባት የገበያ (ግሽበት) መረጋጋት ይፈጥር ይሆን? የኢኮኖሚውን መቀዛቀዝ ከአቶ መለስ ህልፈት ጋር የሚያያይዙትም አሉ፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ? አሁን እኮ የኢኮኖሚም ሆነ የገበያ መረጋጋት የለም፡፡ ሀገሪቱ ከፍተኛ የውጭ እዳ አለባት፣ የብር የመግዛት አቅም ተዳከሟል፡፡ በዚህ ሁኔታ መረጋጋት የሚታሰብ አይደለም፡፡ ሀገሪቱ መመራት ያለባት በሲስተም እንጂ በሰዎች ማንነት አይደለም፡፡ በሰዎች ማንነት የሚመራ ኢኮኖሚ አሁን ላለንበት ሁኔታ አስተዋፅኦ ይኖረዋል፡፡ ያለመረጋጋት እና ከሲስተም ውጪ የሆነ ስራ ነው ውጤቱ፡፡

ኢኮኖሚው በተቀዛቀዘበት፣ ግሽበቱ ባልቀነሰበት ሁኔታ የሀገሪቷ እጣፈንታ ምን ሊሆን ይችላል? አንድ ጊዜ ፓርላማ እያለሁ ትንቢታዊ የሆነ ነገር ተናግሬ ነበር፡፡ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ጀርመን ውስጥ የጀርመን መገበያያ ገንዘብ ወርዶ መሬት ስለነካ፣ አንድ ቲማቲምና አንድ ድንች ለመግዛት ጀርመናውያን በከረጢት ሙሉ ብር እየያዙ ይዞሩ ነበር፡፡ ይኼን ለፓርላማ ስናገር፣ ይኼንና የኛን ሀገር ሁኔታ ምን ያገናኘዋል? የሚል ምላሽ ነበር የቀረበልኝ፡፡ አሁን እንግዲህ ወደዚያ ደረጃ እየደረስን ነው ማለት ነው፡፡ ግሽበት “ሀ” ብሎ ሲጀምር ነው ኢኮኖሚው ብዙ ማስታገሻ መርፌ መወጋት ያለበት፡፡ ልማታዊ መንግሥት ነኝ ለሚል የሚቀርቡ መራራ ክኒኖች አሉ፡፡ ከእነዚያ መራራ ክኒኖች አንዱ የምታወጣውን ወጪ ቀንስ የሚለው ነው፡፡ ያንን መራራ ኪኒን አልውጥም በማለቱ ነው ዛሬ ከዚህ ደረጃ ያደረሰን፡፡ ያንን መራራ ኪኒን ውጦ ወጪውን ቢቀንስና በጀት ቢያጠብ ኖሮ፣ እዚህ አንደርስም ነበር፡፡ አሁንም እነዚህ የቀበቶ ማጥበቅ ስራዎች ካልተሰሩ የሚገነባው ልማት ዝም ብሎ ገንዘብ አትሞ ከማፍሰስ ውጪ በምርታማነት ሊገኝ ስለማይችል ኢኮኖሚው ከፍተኛ ችግር ውስጥ ይገባል፡፡ ይኼ ላይ ላዩን የተቀባባ ነገር እየቀጠለ በህዝቡ ላይ ግን የከተማ ድህነት እየጨመረ፣ የመንግሥት ሠራተኛው በገቢው መተደደር እየተቸገረ፣ ምርት እየጠፋ በሚሄድበት ጊዜ ከፍተኛ የማክሮ ኢኮኖሚ ቀውስ ውስጥ እየገባን ነው የምንሄደው፡፡

ገዢው ፓርቲ አሁን አለች የምትባለውን የኢኮኖሚ እድገት ሊያስመዘግብ የቻለው፣ ከ1997 ዓ.ም በኋላ በወቅቱ “ኦርጅናሉ ቅንጅት” በፈጠረው የሰላማዊ ተቃውሞ ህዝቡ ሌላም አማራጭ አለ ብሎ ማሰቡን መንግሥት ተገንዝቦ ከእንቅልፉ በመንቃቱ ነው፡፡ አሁንም ግን እድገቱ ተገኘ የተባለው ትውልድን ከፍተኛ የውጭ እዳ ውስጥ በማስገባት ነው፡፡ አሁን እኮ መንግሥት ለሁለት ወር የሚበቃ የገቢ እቃ ለማስመጣት የሚያስችል ገንዘብ የለውም፡፡ አንዳንድ ነጋዴዎች ባንክ ውስጥ “ሌተር ኦፍ ክሬዲት” ለመክፈት ቆዩ እየተባሉ ነው፡፡ ሁለተኛ ደግሞ የውጭ እዳው አሳሳቢ ነው፡፡ ለትውልድ የሚተርፍ ተከፍሎ የማያልቅ እዳ ውስጥ እየገባ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በንግድ ከተሻረከቻቸው ሀገራት ጋር በሙሉ ኢ-ሚዛናዊ በሆነ የንግድ ሂደት ውስጥ ነው ያለችው፡፡ ሚዛናዊ ወይም ትርፋማ የሆነ የንግድ ጥምርታ የላትም፡፡ ይኼ መንግሥት እኮ የሱቅ ነጋዴ ቢሆን ኖሮ በአንድ ሳምንት ነው ሱቁን መዝጋት ያለበት፡፡ ምክንያቱም የሚገዛው ከሚሸጠው በእጥፍ የሚበልጥ ነው፡፡ ስለዚህ አንድ ገዢ ፓርቲ በዚህ አይነት ሁኔታ ማስተዳደር አይችልም፡፡

ከዚህ ሁኔታ ውስጥ ለመውጣት ደግሞ አንደኛ ለውጭ ግብይት የሚያቀርበውን ሸቀጥ በአይነት መጨመር አለበት፡፡ ሁለተኛ (Import substitution) የሚባል አለ፡፡ እነዚህ ከውጭ በከፍተኛ ምንዛሬ ተገዝተው የሚገቡትን ተክተን በራሳችን ልንሰራቸው የምንችላቸው ማለት ነው፡፡ ይሄን ለማድረግ የሚችሉ ስራ ፈጣሪዎችን መንግሥት ሊያበረታታቸው ይገባል፡፡ ይኼ እየተደረገ አይደለም፡፡ ስለዚህ መንግሥት ከተቃዋሚ ፓርቲዎችም ጋርም ሆነ ከሌላው ዜጋ ጋር በመመካከር ችግሮች በዘላቂነት የሚቀረፉበትን መንገድ መፈለግ አለበት፡፡ ኢኮኖሚን መገንባት ይቻላል፤ ጤናማ ኢኮኖሚን ለመገንባት ግን የተለየ ሙያዊ ብቃት ይጠይቃል፡፡ ጤናማ ኢኮኖሚ የሚባለው የዋጋ ግሽበትን የተቆጣጠረ፣ ስራ አጥነት እንዲቀንስ የሚያደርግና ብሄራዊ ምርት (GDP) እድገትን የሚያመጣ ነው፡፡ ይሄን ማድረግ ደግሞ ይቻላል፡፡ ከፖለቲካ እይታ ውጪ ብቃቱ ያላቸው ሙያተኞችን አሳትፎ፣ ጤናማ የኢኮኖሚ እድገትን ማረጋገጥ ይቻላል፡፡ መንግሥት በአሁን ሰዓት ከ70 በመቶ በላይ የሚሆነው ኢትዮጵያዊ ከድህነት ወለል በላይ መሆኑንና 30 በመቶው ብቻ በድህነት ውስጥ ያለ መሆኑን እየገለፀ ነው፡፡ እርሶ ይሄን ይቀበሉታል? በመሰረቱ ይኼ ታማኝነት አለው ወይ? የሚለውን ማየት ያስፈልጋል፡፡ ገዢው ፓርቲ ብዙ ጊዜ የሚያወጣቸው መረጃዎች ታሽተው ነው እኛ ጋር የሚደርሱት፡፡

የመረጃ ምንጫችንም ይኸው ገዢው ፓርቲ ብቻ ነው፡፡ ነፃና ገለልተኛ በሆነ አካል ይህን ማረጋገጥ አንችልም፡፡ እኛ ግን አሁን ባለንበት ሁኔታ መጠየቅ የምንችለው፣ የድህነት መጠኑ ወደ 30 በመቶ ወርዷል ከተባለ እንዴት ነው ይሄ ነገር የተፈፀመው? የሚለውን ጥያቄ ነው፡፡ የህዝብ ቁጥር ስለቀነሰ ነው? እንግዲህ የህዝብ ቁጥር በጨመረ ቁጥር ብሄራዊ ምርቱ ለብዙ ህዝብ ነው የሚከፋፈለው፡፡ አሁንም የሚሆነው ፍትሃዊ የሆነ የሀብት ክፍፍል አለ ነው፡፡ አሁን ግን የህዝብ ቁጥር አልቀነሰም፤ መረጃዎች የሚያመለክቱት እንደጨመረ ነው፤ ስለዚህ እንዴት ሆኖ ነው ይኼ ድህነት ቅነሳ ሊመጣ የቻለው? በብሄራዊ ምርት እድገት ነው ከተባለ ደግሞ እድገቱ የከተማ ድህነትን ጨምሯል፡፡ ምክንያቱም የዋጋ ግሽበቱ ትልቁ ቀንበር የሚያርፈው ድሃው ህብረተሰብ ላይ ነው፡፡ ገቢው የተወሰነና ሊጨምር የማይችል ሆኖ የዋጋ ግሽበቱ ግን በልጦታል፡፡ ስለዚህ የከተማ ድህነት እየጨመረ ነው ያለው፣ የገጠሩም በተመሳሳይ ነው፡፡ ከህዝቡ 12.5 ሚሊዮን ያህሉ ከግማሽ ሄክታር በታች ይዞታ ያላቸው ገበሬዎች ናቸው ዝናብ ሲዘንብ ጠብቀው ራሳቸውን መግበው፣ ሌላውን ህብረተሰብ ለመመገብ የሚታትሩት፡፡ ዝናብ ሳይዘንብ ደግሞ እነሱም ተርበው ህብረተሰቡም ይራባል፡፡

ስለዚህ ከድህነት ወጡ የተባሉት የመሬት ይዞታቸው ጨምሮ ነው? ምርታማ ሆነው ነው የሚለውን መመለስ ያስፈልጋል፡፡ እነዚህ 12 ሚሊዮን ገበሬዎች በከፍተኛ ድህነት ላይ ነው ያሉት፡፡ በአለም ባንክ ሪፖርት፤ የገቢ ድህነት ያለባቸው መሆኑ ተገልጿል፡፡ እሱ ብቻ አይደለም፤ የይዞታ ድህነትም አለባቸው፡፡ እነዚህ ገበሬዎች አሁን ላይ ራሳቸውን የሚያዩት እንደመንግሥት ተቀጣሪ ነው፡፡ ምክንያቱም አሁን ያሉበት መሬት መጥበብና ማነስ ብቻ ሳይሆን ያችም ብትሆን በገዢው ፓርቲ ፈቃድ ስር የዋለች ናት፣ የፖለቲካ ጥገኞች ናቸው፡፡ ስለዚህ በምን ምክንያት ነው እነዚህ ሰዎች ከድህነት የወጡት? የመሬት ይዞታቸው ጨምሯል፣ የአስተራረስ ዘይቤያቸው ተሻሽሏል፣ የምርት ግብአቶች ተሻሽሎ ነው ተብሎ መጠየቅ አለበት፡፡ ቀንሷል የሚለው ሪፖርት እውነት ከሆነ ደስ ይለን ነበር ግን በአይናችን እያየነው አይደለም፡፡ ምክንያታዊም አይደለም፡፡ የገዢው ፓርቲ ኃላፊዎች ይሄን ሲናገሩ ምክንያታዊ በሆነ መንገድ ሊያስረዱን ይገባል፡፡ መንግሥት በ2004 የበጀት ዓመት የግብርና ምርቱም ቀንሷል፤ የታሰበውን ያክል አይደለም የሚል መረጃም አቅርቧል፡፡

የግብርና ምርታማነት ማሽቆልቆሉ ከምን ጋር ነው የተያያዘ ነው? እንግዲህ እነዚህ ሰዎች በአንድ በኩል የድሃው ቁጥር ቀንሷል እያሉ፣ በሌላ በኩል የግብርና ምርቱ ቀንሷል እያሉን ነው፡፡ ግን ጥያቄው መሆን ያለበት ይህ ለምን ሆነ የሚለው ነው፡፡ ከግብርና ኢኮኖሚ ወደ ኢንዱስትሪ ገብተናል? ወደ አገልግሎት ዘርፍ ገብተናል? እነዚህ ናቸው ሊነሱ የሚገባቸው፡፡ አሁን ምርት ቀንሷል እያሉን ነው፡፡ ምርት በአስገዳጅነት የሚመጣ አይደለም፡፡ በአዋጅም የሚገኝ አይደለም፡፡ በነፃ ገበያ፣ በፍላጐት፣ በአቅርቦት አርሶ አደሩ የመሬቱ ባለቤት ሲሆን፣ የግል ፍላጐቱ ሲጨምር፣ ራሱን እንደመንግስት ተቀጣሪ ሳይሆን እንደነፃ ዜጋ መመልከት ሲችል፣ ለራሱ ጥቅም ብሎ መንቀሳቀስ ሲጀምር ነው ምርት የሚጨምረው እንጂ ምርት በአዋጅ አይጨምርም፡፡ ዜጐች በነፃነት ሲንቀሳቀሱ ብቻ ነው ምርት ሊጨምር የሚችለው፤ በትክክል ነገሩ የገባቸው አልመሰለኝም፡፡

ገዢው ፓርቲ ለህዝብና ለሀገር የሚበጁ ደንቦችን ማውጣት ነው እንጂ እዚህ ጋ ስንዴ እዚያ በቆሎ ቀንሱ ብሎ ገበያ ውስጥ ገብቶ የሚያተራምስበት ስርአት እኛ የምናውቀው የለም፡፡ በዚህ መንገድ ደግሞ አንድ አውራ ገዢ ፓርቲ ከማዕከል እስከ ቀበሌ ያስተዳድራል፡፡ ኢኮኖሚውንም እኔ በምለው መንገድ አስተዳድራለሁ በማለት ወደ ባሰ ችግር ውስጥ እያስገባን ነው፡፡ አሁን ጠቅላይ ሚኒስቴሩ የሚሉት ነገር የእሳቸው የአስተዳደር ስራ አይደለም፡፡ በእርግጥ አበዳሪ ድርጅቶችና ሀገራት እንደሚናገሩት አይነት የገበያ ስርአት የምንመሰርት ከሆነ ይኼ የገበያው ድርሻ ነው፡፡ ይሄን በ18ኛው ክ/ዘመን ነው አዳም ስሚዝ የተናገረው፡፡ በዚህ ነው የነፃ ገበያ ስርአት የሚተዳደረው እንጂ በአዋጅ አይደለም፡፡ በአዋጅ ሲተዳደር ነው አሁን ያለበት ቀውስ ውስጥ የምንገባው፡፡ ስኳር በዚህን ያህል ዋጋ ትገዛለህ፣ ጤፍ ከዚህ ቦታ ትገዛለት ሲባል ችግር አለው፡፡

ከፍተኛ መተራመስ የሚያመጣ ኢኮኖሚውን ለማረጋጋት የማይችልበት አዘቅት ውስጥ የሚያስገባ ነው፡፡ የግብርና ምርታማነት እንደታሰበው አለመሆኑ በአቅርቦት ላይ የሚፈጥረው ተፅእኖ እንዴት ይታያል? ከወራት በፊት በሰማሁት ሪፖርት የግብርና ምርታችን በ5 በመቶ ጨምሯል ብለው ነበር፡፡ አሁን ምርት ከአይን እየጠፋ በመምጣቱ እንደገና ቀንሷል እያሉን ነው፡፡ የቀሰነበትን ምክንያትም በትክክል አያውቁትም፡፡ የዛሬ ዓመት ፓርላማ በነበርኩ ጊዜ የዋጋ ግሽበት ምክንያቱ በጥናት መታወቅ አለበት ብዬ እየጠየቅሁ ነበር፡፡ አሁንም ምርት ጨምሯልም ቀንሷልም ሲሉ ምክንያት የላቸውም፡፡ ከጥቂት ካድሬዎች የሰሙትን ወሬ እያስተጋቡ ነው፡፡ መሰረታዊ የሆነ የምርምር ውጤት ቢኖራቸው ኖሮ የዛሬ ሁለት ወር በ5 በመቶ ጨምሯል የተባለው አሁን ቀንሷል ሊባል አይችልም ነበር፡፡

ይሄ የምርት መቀዛቀዝና የገበያ አለመረጋጋት በህዝብ ዘንድ ሰቆቃ ሊያመጣ፣ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ቀውስ ሊያስከትልና ዜጐችን አደጋ ላይ ሊጥል የሚችል ነው፡፡ አሁንም ቢሆን ይሄ ገዢ ፓርቲ የማክሮ ኢኮኖሚ አስተዳደሩን ለመምራት ከፍተኛ ችግር አለበት፡፡ ከፖለቲካ አመለካከት የፀዱ ባለሙያዎች የማግኘት ችግር አለበት፡፡ ከዚያ ውጪ ይሄንን ነገር ለማየት ካልተቻለ በአብዮታዊ ዲሞክራሲና በአንድ ገዢ ፓርቲ አመለካከት ብቻ ይሄን ሰፊ ሀገርና 90 ሚሊዮን ህዝብ አረጋግቶ ለመምራት ያስቸግራል፡፡ እርሶ ፓርላማ በነበሩ ጊዜ ስለፊሲካልና ሞኒተሪ ፖሊሲ ደጋግመው ሲናገሩ ይደመጡ ነበር፡፡ ይሄ ነገር ለአብዛኛው ሰው ግልፅ አይደለም፡፡ ሞኒተርና ፊሲካል ፖሊሲ ማለት ምን ማለት ነው? በእውነት ይሄን ጥያቄ በደንብ ማብራራት የምፈልገው ጉዳይ ነው፡፡ ባለፈው ጊዜም ሆነ አሁን ያለው የሞኒተሪና ፊስካል ፖሊሲ አመራር በከፍተኛ ሁኔታ ስሜቴን የሚነካኝ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ እነዚህን ሃቀኛ በሆነ መንገድ ለማስተዳደር ባለመቻሉ፣ የኢትዮጵያን ህዝብ የኢኮኖሚ ችግር ላይ ጥሏል፡፡

ማክሮ ኢኮኖሚ አስተዳደር ላይ ችግር የፈጠረውም በዚሁ ምክንያት ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ በፊሲካል ፖሊሲው ግብር የመጣልና የመሰብሰብ፣ አዲስ ግብር ከፋዮችን ማካተት፣ ፍትሃዊ የሆነ የግብር ስርአት እንዲኖር ማድረግ… እነዚህ ሁሉ የስራ አስፈፃሚው ኃላፊነቶች ናቸው፡፡ ፊሲካል ፖሊሲ የሚባለው ይሄ ነው፡፡ አንድ ኃላፊነት የሚሰማው ገዢ ፓርቲ በሚሰበስበው ግብር ይተዳደራል ማለት ነው፡፡ ሁላችንም በገቢያችን መጠን ለመተዳደር እንደምንሞክረው ማለት ነው፡፡ ከገቢያችን በላይ የምንተዳደር ከሆነ ችግር አለ ማለት ነው፡፡ በፊሲካል ፖሊሲው ያልሰበሰበውን ወይም ያላመረተውን እየበላ ያለው ገዢ ፓርቲ ነው፡፡ ይሄ እንዴት ነው የሚገለፀው ከተባለ፣ ወደ 12 ቢሊዮን ዶላር የውጭ እዳ አለበት፣ የበጀት ጉድለቱ ከገቢው በላይ እየተዳደረ መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡ የሀገሪቱ ብር የመግዛት አቅም የመጨረሻው ደረጃ ላይ ነው፡፡ ፊሲካል ፖሊሲውን በተገቢው መምራት ያለበት ገዢው ፓርቲ፣ ይሄን በስርአቱ መምራት ሳይችል ሞኒተሪ ፖሊሲውንም ተቆጣጥሮታል፡፡ ብሄራዊ ባንክ ነፃና ገለልተኛ ሆኖ ነው ሞኒተሪ ፖሊሲውን መምራት ያለበት፡፡ ያ ማለት ብሄራዊ ባንኩ ወደ ኢኮኖሚው ውስጥ የሚገባ የገንዘብ መጠንን ያውቃል፡፡ ዜጐች በቁጠባ ሂሳባቸው ምን ያህል ወለድ ማግኘት እንዳለባቸው ያውቃል፡፡ ያ ዜጐች ያስቀመጡትን ገንዘብ በምን ያህል ለኢንቨስተሮች ማበደር እንዳለባቸው ያውቃል፡፡

ስለዚህ ከስራ አስፈፃሚውና ከህግ አውጭው ተፅእኖ ነፃ ሆኖ መምራት አለበት፡፡ ለምሳሌ በአሜሪካ ፌዴራል ሪዘርቭ ቦርድ የሚሉት ነገር አለ፡፡ ይኼ ቦርድ በነፃነት ከገዢው ፓርቲና ከህግ አውጪው ቁጥጥር ውጪ ወደ ኢኮኖሚው የሚገባውንና የሚወጣውን የገንዘብ መጠን - የወለድ መጠን፣ የባንክ ሪዘርቭ መጠንን ቦንድ ሲሸጥ የሚከፈል የወለድ መጠን… እነዚህን ሁሉ በሞኒተሪ ይቆጣጠራል፡፡ አሁን ይሄን በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ ብናመጣው ሁለት ነፃና ገለልተኛ የሆኑ አካሎች አሉ፡፡ አንዱ ስራ አስፈፃሚው ነው፤ ፊሲካል ፖሊሲውን የሚመራው፡፡ ሌላው ሞኒተር ፖሊሲውን የሚመራው ብሄራዊ ባንክ ነው ማለት ነወ፡፡ እነዚህ እየተነጋገሩ፣ እየተወያዩ ሚዛናዊና ፍትሃዊ ኢኮኖሚ እንዲኖር ያደርጋሉ ማለት ነው፡፡ አሁን ግን እየሆነ ያለው ጨርሶ ሊጠግብ የማይችለው ስራ አስፈፃሚው፤ ብሄራዊ ባንኩን ብር አትም ይለዋል፣ በራሱ ተፅእኖ ስር የወደቀ ብሄራዊ ባንክ ደግሞ ደሞዙን የሚከፍለው ማን እንደሆነ ስለሚያውቅ የሚፈልገውን ያክል ያትምለታል፡፡ ኢኮኖሚው ግን ያንን ሊሸከም አይችልም፡፡

ስለዚህ ማነው ዋጋ እየከፈለ ያለው? ስንል የኢትዮጵያ ሸማቹ ህዝብ ነው፡፡ እንግዲህ በግልፅ ለማስቀመጥ ፊሲካል ፖሊሲ የምንለው፣ የግብር አሰባሰብና አጠቃቀም ሲሆን ሞኒተሪ ፖሊሲ የምንለው የብሄራዊ ባንኩን ተግባራት የሚያመላክት ነው፡፡ የግብር አሰባሰቡን ማስፋት አለበት ሲባል እንዴት ነው? አሁን ከትናንሽ ነጋዴዎች ላይ ሳይቀር ታክስና ግብር እየተሰበሰበ ነው… እንግዲህ የእኔም ፓርቲ ቢሆን ስልጣን ሲይዝ ግብር ማስከፈሉ አይቀርም፡፡ ግብር ለልማት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው፡፡ አስፈላጊም ነው፡፡ ዜጐች ፍትሃዊ የሆነ ግብር መክፈላቸው የሚደገፍ ነው፡፡ አሁን ችግር እየሆነ ያለው የተሰበሰበው ግብር ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ለልማት እየዋለ ነው? የሚለው ነው፡፡ ግን እንደዚህ አይነት የግሽበት አጋጣሚ ውስጥ ስንኖር ገዢው ፓርቲ ግብር የሚከፍሉትን ብቻ ከፍተኛ ተፅእኖ ውስጥ እንዲወድቁ ማድረግ ሳይሆን የማይከፍሉት እንዲከፍሉ መረቡን ማስፋት ነው ያለበት፡፡

ሁሉም የዜግነት ግዴታውን እንዲወጣ ማድረግ ነው ያለበት እንጂ የተወሰኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን እንዲጐዱና ለመኖር እንዳይችሉ ማድረግ አይደለም፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ግን ህዝቡ እያማረረ ያለው ይሄንን ነው፡፡ ፍትሃዊ ባልሆነ ሁኔታ ግብር ተጣለብን ነው ምሬቱ፡፡ ይሄ ደግሞ ግልፅ በሆነ መንገድ የግብር አጣጣልና አሰባሰብ ሊታይ ይገባል ወደሚለው ይወስደናል፡፡ ድብቅ መሆን የለበትም፡፡ ሌላው ይሄ ገዢ ፓርቲ ማፅዳት ያለበት ሙስናን ነው፡፡ በተለይ ከዚህ ከግብርና ከሌሎች ነገሮች ጋር በተያያዘ ዛሬ ከፍተኛ ሙስና እየተፈፀመ ነው፡፡ በ2009 እ.ኤ.አ ወደ 15 ቢሊዮን ዶላር ከዚች ደካማ ሀገር ወደ ውጭ ወጥቷል የሚል ሪፖርት ቀርቦ ነበር፡፡ ይሄ የገዢው ፓርቲ ባለስልጣኖች ሊያፀዱት የሚገባ ተግባር ነው፡፡ እነሱ የሚነግሩን እዚህ ቦታ የ5 ሺህ ብር ሙስና ተፈፅሟል የሚለውን ነው፡፡ እኛ ግን ማወቅ የምንፈልገው ትላልቆቹን አሳዎች ነው፡፡ ከተማ ውስጥ ያሉት የገዢው ፓርቲ ትላልቅ ባለስልጣኖች ምን እያደረጉ እንዳለ ህብረተሰቡ ያውቃል፤ የማን ህንፃ እንደሆነ፣ የትኛው የገዢው ፓርቲ አመራር ቦታ እንደሆነ ያውቃል፡፡ ስለዚህ ቤቱን የማፅዳት ስራ ከራሱ መጀመር አለበት፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን፤ አንድ ሰው፣ ለወዳጆቹ የሚከተለውን ደብዳቤ ፃፈ፡፡ ኑ አቃብሩኝ ዛሬ የጥንቱ የጠዋቱ ወዳጃችን አቶ “ማኅበራዊ-ብስለት” (Common Sense) የቀብሩ ሥነ ስርዓት ስለሚካሄድ ቀብር ላይ ተገኝታችሁ አብረን እንቀብረው ዘንድ ጥሪዬን አቀርባለሁ፡፡ እንደምታውቁት አቶ “ማህበራዊ-ብስለት” የሁላችንም የረዥም ጊዜ ወዳጅ ነው፡፡ ዕድሜውን ማንም አያውቅም፡፡ ምክንያቱም ከልጅነቱ ጀምሮ በቢሮክራሲው ቀይ-ጋዲ (bureaucratic red tape) በየጊዜው እየተተበተበና እየታሠረ በመኖሩ ነው፡፡ ትቶልን የሄደው ቅርስ ግን አይረሴ ትምህርት ነው፡፡ ይኸውም፡- ከዝናብ መቼ መውጣትና መጠለል እንዳለብን በጠዋት የተነሳች ወፍ በጊዜ ቀድማ ትል መያዝና መብላት እንደምትችል ህይወት ሁሌ አልጋ በአልጋ እንዳልሆነችና ሁሌም ሚዛናዊ ሆኖ እንደማናገኛት ምናልባት ጥፋቱ ከኔ ነው ብሎ ማሰብ እንደሚገባ፡፡ “ማኅበራዊ-ብስለት” በህይወት ሳለ፣ ህይወትን ቀለል አድርጎ የሚያይ ከመሆኑም በላይ፤ “ከምታገኘው በላይ አታውጣ! አታጥፋ” የሚል የፋይናንስ ስትራቴጂ እየተከተለ ነበር የሚኖረው፡፡

በተጨማሪም አዋቂዎች እንጂ ልጆች ኃላፊነት እንደሌለባቸው እንድንገነዘብ አስተምሮናል፡ “ማኅበራዊ - ብስለት” ጤንነቱ ድንገትና በፍጥነት መታወክ የጀመረው ለመልካም ታስበው የተፀነሱት ህግጋትና ደምቦች ከታወጁ ቀን ጀምሮ ነው፡፡ ይኸውም፤ አንድ የ6 ዓመት ህፃን የክፍል ጓደኛውን ፆታዊ ጥቃት አድርሶባታል ተብሎ ሲከሰስ፣ አስተማሪ ተማሪ አባረረ ተብሎ ሲከሰስ፣ ወላጆች ልጆቻቸውን በግብረ-ገብነት ገርተው መያዝ ሲገባቸው፤ አስተማሪዎችን ሲወቅሱ፤ ወላጆች የተማሪዎችን የፀጉርና የፊት-ቅባት አጠቃቀምን፤ እንዲሁም የአስፕሪን አዋዋጥን በተመለከተ የምክር አገልግሎት ያገኙ ዘንድ ት/ቤት ድረስ ሲጠሩ፤ ያም ሆኖ ሴት ልጃቸው ማርገዝዋንና ማስወረድ እንደሚያስፈልጋት ሳይነገራቸው ሲቀሩ፤ “ማኅበራዊ-ብስለት” ታሞ አልጋ ላይ ዋለ! እጅግ በሽታው የባሰበትና መኖር ያስጠላው ደግሞ፤ ቤተክርስቲያኖች የንግድ ቦታ ሲሆኑና ወንጀለኞች ወንጀል ከተፈፀማባቸው፤ ከተበዳይ ወገኖች ይልቅ፤ ምቾትና እንክብካቤ ሲደረግላቸው ሲያይ ነው፡፡ ህይወት እጅግ በጣም ከፍታ ውጪ-ነብስ፣ ግቢ-ነፍስ የሆነበት ደግሞ፤ ዘራፊ ወሮ-በላ፤ ሰው ቤት ገብቶ ባለቤቱ መከላከል ሲያቅተውና ዘራፊው ራሱ ዘርፎ ሲያበቃ፣ ራሱ ከሳሽ ሆኖ ሲገኝ ነው! በመጨረሻ ፍፁም ተስፋ የቆረጠውና ለጣር የበቃው ግን፤ በአሁኑ ዘመን፣ እንፋሎቱ እየተነነ ያለ ቡና ትኩስ መሆኑን መገመት ያቃታት ሴት ሲያይ ነው፡፡

ትንሽ እጭኗ ላይ ጠብ ስታደርግ ዋጋውን አገኘች!! “ማኅበራዊ ብስለት” ሲሞት፤ አምስት ልጆቹን እዚህ አገር ትቶ ነው የሄደው፡፡ ሦስቱ የእንጀራ ልጆቹ ናቸው፡፡ ስማቸውም - (የመጀመሪያው) መብቴን አውቃለሁ (ሁለተኛው) አሁኑኑ እፈልገዋለሁ (ሦስተኛው) ጥፋተኛው ሌላ ሰው ነው (አራተኛው) እኔ ተበዳይ ነኝ (አምስተኛው) ምንም ሳልሠራ ክፈለኝ፤ ይባላል፡፡ ብዙ ሰዎች ቀብሩ ላይ አልተገኙም፡፡ ምክንያቱም “ማኅበራዊ-ብስለት” መሞቱን አላወቁም፡፡ አሁንም “ማኅበራዊ-ብስለትን የምታስታውሱት ካላችሁ ይህንን ልቅሶ ላልሰሙ አሰሙ፡፡ ካልሆነ፤ ከብዙሃኑ ጋር ምንም ሳትሠሩ፣ እጃችሁን አጣጥፋችሁ ተቀመጡ፡፡ የጥንት ወዳጃችሁ በማናቸውም ህይወታችን ረገድ፣ በየእርከኑ ከሚያጋጥመን ውሽንፍር-አዘል ዝናብ የምናመልጥበትና የምንጠለልበት ልዩ ብስለት ያሻናል፡፡ ጊዜን ለይተን፣ በጠዋት ነቅተን፣ ግባችንን ለመምታት የጧት - ተነሽ (ማላጅ - Early – riser እንዲሉ) መሆን ይገባናል፡፡ ዘርቶ፣ አጭዶ፣ ወቅቶና ጐተራ ከቶ፣ ከዚያም አብስሎና ቆርሶ፣ የሚያበላንና የሚያኖረን ከራሳችን በቀር ማንም የለም፡፡ የባዕድ አንጐል እንጂ የባዕድ እጅ ማየት የለብንም፡፡ የመተሳሰብ፣ የመቻቻል፣ የመማማር ክህሎት መጀመሪያ አንቀጽ፤ እኔ ተሳስቼስ ቢሆን? የማለት ትሁት ብስለት ነው፡፡

“ተጣልቶ ለመታረቅ የማይችል ወይም የማይሻ፤ ካብ - አይገባ - ድንጋይ ነው፡፡ ሳይጣላ የሚታረቅም ያለዕዳው ዘማች ነው” ይላሉ አበው፡፡ አንድ ብስለት ይሄን ማወቅ ነው፡፡ የብስለት ሌላኛው እጁ ሰው ከሰው መቻቻሉ ነው፡፡ ሎሬት ፀጋዬ በ”ነይ መርካቶ” ግጥሙ እኒህን መስመሮች ለግሶናል-እንድንቻቻል፡- “በአራዳው ጊዮርጊስ ፈረስሽ፣ ተንጠራርተሽ እስከአንዋር “ኪራራ ይሶን” ጥሪሽን፣ አሸጋግረሽ “በአላህ አክበር” በአባ መቻል ላይ ድልድይሽ፣ ታጅበሽ እስካማኑኤል ዳር በአባ መቻል ላይ ድልድይሽ፣ ታጅበሽ እስካማኑኤል ዳር መርካቶ ነይ እንደገና፤ ፀሎታችን ይታደግሽ ምርቃታችን ያካብትሽ፣ የከርታቶች መጠለያ መርካቶ ያዲሳባ አድባር ከሰባት ቤት ጉራጌሽ ቤት፣ ከኦሮሞሽ አውድማ ዳር ከወሎሽ ጀበና መጀን፣ ከጊሚራው በርሽ አፋር ከአማራሽ የሰብል አውጋር፣ ከጎጃም በረንዳሽ ግንባር እንደገና ነይ መርካቶ፡፡ ሌላው ብስለት የወራሽና አውራሽ መንገዳችን ነው፡፡ አዲሱ አሮጌውን መተካቱ፣ ገፍቶ መጣሉ ወይም ከናካቴው ማጥፋቱ፤ ያለና የነበረ ዲያሌክቲካዊ ሀቅ ነው፡፡ “በሕግ አምላክ”፣ “በንጉሥ አምላክ!” ብሎም ቢሆን፤ መግፋት የተለመደ ነው፡፡

“ወድቆ በተነሳው ነው ተነስቶ በወደቀው ባንዲራ የሚባለው?” ትላለች አንድ የሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን ዕብድ ገፀ-ባህሪ! ስለመተካካት ስናስብ አንድ አንድ መሠረታዊ ነቁጦችን ልብ እንበል፡፡ “ከአንተ ቀድሞ በነበረው ባለሥልጣን ወይም አባት ሰው፤ የተለየሁ ነኝ ብለህ ታምን ይሆናል፡፡ ሆኖም እያደግህ ስትሄድ እስከወዲያኛው ቆራጥ ካልሆንክ ተፃርረኸውና አምፀኽበት የነበረውን አባትህን ትሆናለህ” ይላል አንድ የፖለቲካ ፀሀፊ፡፡ አባትህን መተካት በአያሌው ያንተን ፅንዓት ይጠይቃል፡፡ የሚያስከፍለው ዋጋ አለ፤ ሲል ነው፡፡ “ውሎ አድሮ አንተ የራስህን አባት መሆንህን አትርሳ! ስለዚህም ዞረህ ዞረህ መከላከያህን መክነህ፣ ጭምብልህን አውልቀህ ያው የትላንቱ ጣረ-መንፈስ ማለትም፤ አባትህ፣ ልማድህና ታሪክህ-መልሶ መምጣቱ ላይቀር፤ ሌላ አንተነትህን ለመፍጠር ስትፍጨረጨር ዕድሜህን አትፍጅ” የሚለውን አፅንዖት ይሰጠዋል ያው ፀሀፊ፡፡ ሆኖም አንድን ዕውነት ዋና መልሕቅ አድርጐ ጠንካራ አደራ ያሰፍራል፡፡

በግጥም ስናስቀምጠው የቁም ነገሩ ቡጥ የሚከተለው ነው፡፡ “አየህ፤ ከትላንትህ ተጋጭተህ፣ ትላንትናህ ላይ አምፀህ ጉልላት አናት የወጣህ፤ ግርጌህ ያሉትን አትርሳ፤ ከቶም ዐይንህን አትንቀል አመፃ ያንተው ቅጂ ነው፣ በተከሉት የሚተከል! ይነሳሉ፤ ያው እንዳንተው አንድም ዕድል አትስጣቸው፤ ካይንህም አታርቃቸው ወንድሜ ዕንቅልፍ አይጣልህ፣ መንገዱ ያንተው መንገድ ነው!!” በሀገራችን ረጅም የፖለቲካ ሂደት ውስጥ አንዳንድ ከመሠረቱ የተበላሹ ስህተቶች እንደጥቁር ጥላ ይከተሉናል፡፡ እንደ ዲሞክራሲ፤ እንደ ኤትኒክ-ፌዴራሊዝም፣ ስለ ጠረጴዛ ውይይት፤ ማለትም ስንታረቅና ስንጣላ፣ ስንደራደርና ስንግደረደር ብስለት ለማጣታችን፣ እንደምርጫ፣ እንደ ዕርቅና ሽምግልና ያሉ፤ አንጓ አንጓ ጉዳዮች ከነእንከናቸው ያሳድዱናል፡፡ መሻሻል፣ መቃናት፣ ፈር-መያዝ አለባቸው፡፡ “አሳማ ነው እንጂ ጨዋ ወደ ትፋቱ አይመለስ” ይላል ገጣሚው፡፡ ከውሉ፣ ከመሠረቱ ያለውን መርምሮ፣ “ካፈርኩ አይመልሰኝ” ሳይሉ፤ ማቃናት ደግ ነው፡፡ ለዚህም፤ “ስልቻ ተበላሸ፡፡ ምኑጋ? ሲነፋ፡፡ ሲነፋ አይደለም፡፡ መጀመሪያ ሲገፈፍ ነው”፤ የሚለውን ተረትና ምሳሌ ልብ ማለት መልካም ነው፡፡

ዛሬ ማንም ጋዜጣ ላይ የጻፈ ሰው፤ ነገ መጽሃፍ ይዞ እንደሚመጣ እርግጠኛ እስከመሆን ደርሰናል፡፡ ይሄ ደግሞ “ደራሲ” የሚለውን ብርቅ ስም ያለአቅም ለመሸከም ምክንያት እየሆነ መጥቷል፡፡ ፖለቲካ የጻፈው፣ ስለሳይንስ ያወራው፣ ሁሉም ከጋዜጣ ወደ መጽሃፍ መሸጋገሩ ተለምዷል፡፡ ይህ ልምድ ደግሞ የኛ ብቻ አይደለም፡፡ በተለይ ያደጉት ሃገራት ደራሲያን ይህንን ሲያደርጉት ለመኖራቸው በጄ ላይ ያሉ መጽሃፍት እማኝ ናቸው፡፡ በጋዜጣ ላይ የወጡ ብቻ ሳይሆኑ በሬዲዮ የተተረኩና በቴሌቪዥን የታዩ ፕሮግራሞች ሳይቀሩ ታትመው ለህዝብ ቀርበዋል፤ይሁንና ውስጣቸው ሲታይ ግን እንቶ ፈንቶ አይደሉም፡፡ ለምሳሌ ዴቪድ ፍሮስት የተባሉ የቴሌቪዥን ጋዜጠኛ የጻፉት መጽሃፍ ቀላልና ተራ ነገር የያዘ ሳይሆን ታላላቅ የአሜሪካ የኪነጥበብና የፖለቲካ እንዲሁም የህግና የሌላም ሞያ ባለቤቶችን ያካተተ በመሆኑ የሚሰጠው ዕውቀት ቀላል አይደለም፤ለምሳሌ የማርቲን ሉተር ኪንግ ያልተነገሩ ነገሮች በጓደኛው አማካይነት ተጽፈው ቀርበዋል፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ የተለያዩ ደራሲያን የጻፏቸው መጣጥፎች ተሰባስበው ታትመዋል፡፡

ለዚህ ምሳሌ የሚሆኑን የፐርልስ በክና የሌሎች የስነጽሁፍ ምሁራን ስራዎች ናቸው፡፡ የተለያዩ ደራሲያንን ቃለምልልስ የያዘው የቻርልስ ሩአስ “conversations with American writers” የተሰኘ መፅሐፍ ተጠቃሽ ነው፡፡ ወደ እኛ ሃገር ስንመጣ ግን እውነታው ሌላ ነው፡፡ በእርግጥ ጊዜ የማይሽራቸው ፣የታላላቅ ሰዎችን ታሪክ የያዙ ወይም ደግሞ እንደ ጲላጦስ “ፍልስፍና” ዓይነቶቹ በመፅሐፍ መልክ መታተማቸው ጥሩ ነው፡፡ ምክንያቱም እነዚያ ጸሃፊው ደክሞ የሰራቸው ሃሳቦች በቀላሉ ዳግም ስለማይገኙ፣ የዚህ ዓይነት ስራዎችን ማሳተም ለትውልድ እንደማስተላለፍም ይቆጠራል፡፡ዕውቀት ሆነው ለትውልድ የሚተላለፉ ከሆነ ደግ ነው፡፡ ከዚያ ውጪ ከሃሜት ያልተለዩ ፅሁፎችን፣ በጥላቻና በቂምበቀል የተሞሉ ፖለቲካዊ የጋዜጣ ፅሁፎችን በመፅሐፍ ማሳተም ግን ጥጃዋ ለሞተባት ላም ፣ ጭድ የተወተፈበት ቆዳ በማቅረብ ወተት እንድትሰጥ እንደማታለል ነው፡፡

ላም እንስሳ ስለሆነች የሟች ጥጃዋን ቆዳ ገፍፈው ጭድ በመክተት ሲያቀርቡላት ጡትዋን ትሰጣለች ፤ እኛ ግን ሰዎች ነን - ለዚያውም አንባቢ! አንባቢ ደግሞ የተሻለ መመዘኛ አለው ብዬ አምናለሁ፡፡ አሁን አሁን ግን እኛ ጋ የአንድ ሰሞን የፖለቲካ ትኩሳት፣የሚያልፍ ገጠመኝ ወዘተ ይዘን “አረ ጎራው” እንላለን፡፡ ወይም ለሽቀላ እንነሳለን፡፡ እንደኔ እንደኔ በተለይ እንደበዕውቀቱ አይነት አዳዲስ ሃሳብ ብቅ የሚልባቸው ወጎችና ጽሁፎች እንዲታተሙ መፈቀድ ብቻ ሳይሆን ገንዘብ ያለው ጥበብ ወዳድ ቢኖርና ቢያሳትመው ደስ ባለኝ ፤ክፋቱ የኛ ሃገር ድርጅቶች ስፖንሰር የሚያደርጉት ምናልባት እግር ኳስን እንጂ ጥበብ ብዙም አይማርካቸውም፡፡ ለነገሩ ጥበቡም አላማረበትም፡፡ ውበት እየተረሳ ፣ ሽቀላ ብቻ እየነገሰ መጥቷል፡፡ ብር ከሰውም ከጥበብም ይልቅ ሃገር እየገዛና እየሸጠ ያለበት ዘመን ቢኖር ዛሬ ነው፡፡ አውጣን እያሉ ከመታገል ውጪ ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡

ጋዜጠኞቻችን እጅግ በሚያሳፍር ሁኔታ ለብ ለብ ናቸው፡፡ ሌላው ቀርቶ ሳምንታዊ ጋዜጣዎችን የሚያነቡ ስንት ናቸው ብትሉ እፍኝ አይሞሉም፡፡ ስለዚህ ስለንባብና ስለጥበብ ያላወቀ “ነጋዴ ጋዜጠኛ” ስነጽሁፍ ሲወድቅና ሲነሳ ምን ስሜት ሊሰጠው ይችላል? ቀድሞ ራሱ ወድቋልና፡፡ምናልባት እንደጋንዲ ያለ ሰው ያስፈልገን ይሆናል፡፡ ግን ከየት ሊወለድ ይችላል? ጋንዲ ያልኩት ጥበብ እንዲያሳድጉ የተሰጣቸውን ስልጣን፤ አዙረው ለሌላ ፖለቲካዊ ጥቅም ለመመንዘር የሚተጉ ሰዎችን ስላየሁ ነው፡፡ ጥበቡን ሸጠው እንጀራና ስልጣን የሚያሳድዱ ሰዎችን ማየታችን እንግዳ አይደለም፡፡ ለዚህ ነው የጥበቡ ሰፈር ጭርታ የበዛበት! አሜሪካዊቷ የወግና መጣጥፍ ጸሃፊና ደራሲ ማርጋሬት ሲ ባኒንግ እንደሚሉት፤ በጋዜጣ ላይ የሚወጡ ተከታታይ ጽሁፎች ለፈጠራ ደንቃራ ናቸው፡፡ እንዲያውም በጋዜጣ ላይ በተከታታይ የሚታተሙ ልቦለዶች እንኳ የረዥም ልብወለድ (ኖቭል) እንጀራ ልጆች ናቸው፡፡

ጥበብ በሚገባ እንዳያድግ መንገድ የሚይዙ፡፡ እናም በስነጽሁፍ አለም ውስጥ ምንም አክብሮት አይሰጣችውም፤ወይም ግርማ የላቸውም ይላሉ - ደራሲዋ፡፡ እርሳቸው በሚጽፉበት የሴቶች ጉዳይ ላይ ያተኮረ መጽሄት፤ የዚህ ኣይነቱን ጽሁፍ ክፉኛ በመተቸቱ፣ አሁን አሁን አቅም እያጣ እንደመጣ ይናገራሉ፡፡ እኛ አገር ግን ትችትና ሂስ እየተዳከመ በመምጣቱ ሁሉም የፈለገውን እየፃፈ የሚያሳትምበት ጊዜ ላይ ደርሰናል፡፡ የጋዜጣ ላይ ጽሁፎች መጽሃፍ ላይ መታተማቸውን አስመልክቶ አንድ ጸሃፊ ከጥቂት ወራት በፊት የጻፉትን ጽሁፍ አንብቤ ነበር፡፡ ይሁንና ሙሉ ለሙሉ ተቃውሞ ብቻ ስለነበር ፣ ግለሰቦች ላይ ያነጣጠረና አሁንም “ሸቀጣዊ” አስተሳሰብ ያለው ስለመሰለኝ በአክብሮት ልቀበለው አልቻልኩም፡፡ በርግጥ ጽሁፉ የሚያሳያቸው እውነታዎች አሉ፡፡ ጥቅል ሃሳቡ የጋዜጣ ላይ ጽሁፎች ህትመት ሲበዛ፤ አንባቢው አዳዲስ ስራዎች አያገኝም የሚል ነው፡፡ የበዕውቀቱንና መሰል ፀሃፍትን ጽሁፎችም ጠቅሶ ነበር፡፡ ግና መስመር ያለማበጀቱ አናደደኝ፡፡ እንዴት ነው የበዕውቀቱ ወጎች ከሌሎች የጋዜጣ ጽሁፎች ጋር በጅምላ የሚተቸው?የእሱ ቀልዶች እኮ ሰማይ ቀድደው ያያሉ፡፡ “የአስተናጋጁ ማስታወሻ” ላይ ያነበብኩት አንድ ታሪክ ሁሌ ይገርመኛል፡፡

ሲቀልዱ ሰውን ማሳቅ ብቻ ሳይሆን በጥልቀት እንዲያስቡ ማድረግ እንደሚቻል በዕውቀቱ አሳይቷል፡፡ አንድ የቆሰለ ሰውዬ ቀይ ቀበሮ ቁስሉን ስትበላው አይቶ፣ ባለጠመንጃው ሊተኩስ ይሞክርና ቀይ ቀበሮ መሆንዋን ያያል፣ያኔ ጠመንጃውን መለስ ያደርጋል፡፡ ለካ እኛ ሃገር ቀይ ቀበሮ ከሰው ይልቅ ውድ ነው!... ደሃ ስለሆንን ከሰው ይልቅ ለሰው የሚያስፈልጉት ነገሮች ናቸው! እንዲህ መሰል ነገሮችን የጻፈው በዕውቀቱ፣ ደጋግሞ ቢጽፍና ቢያሳትም ከዳቦዬ ቆርሼ ከመግዛት ወደ ኋላ አልልም፤ አልቆጭም፡፡ ለአለማየሁ ገላጋይ ፅሁፎችም ያለኝ አመለካከት ከዚሁ ጋር የተመሳሰለ ነው፡፡ ውብ የቋንቋ አጠቃቀምና ጥሩ ሃሳብ የመምረጥ አቅም አለው፡፡ ስሜትና ወሬ ብቻ ይዞ አይጋልብም፡፡ አንዳንዴ ሊያነቅፈው ቢችልም ጎበዝን ሲሳሳት መታገስ ያስፈልጋል፡፡ ከሺህ “ኮተታሞች” አንድ ጥርት ያለ ይሻላል፡፡ የግጥሙ ሰፈር የተበለሻሸው በዚህ የተነሳ ይመስለኛል - ሺ “ኮተታሞች” አደባባይ ላይ ብዙ ሳይደክሙ መታየት ስለሚፈልጉና “መጽሃፍ አሳተመ” መባልን እንደ ገድል ስለሚቆጥሩት፡፡ አሁንም የጋዜጣ ጽሁፎች አንዱ ሩጫ ያልተወለዱበትን ተልዕኮ ለማሳካት የሚደረግ መታተር ነው፡፡ ያለመክሊት ስም መፈለግ!... አንዳንዶቹ ለንጹህ ሽቀላ ሲሆን፣ ሌሎቹ ለስም ነው - ”ደራሲ” ለመባል ያላቸውን ናፍቆት ለመወጣት፡፡ ተፈጥሮና ፈጣሪ ካልሰጡኝ ቢቀርስ!... በቃ መጣጥፍ ጸሃፊ ብሆን! ህሊና ሲኖር ይህ ይቻላል፡፡ አንዳንዶቹማ የሰዎችን ስም መጥራት ሲቀራቸው ስድባቸውን በመጽሃፍ ማሳተም ጀምረዋል፡፡

ምነው ጎበዝ! የሃገራችንን ስነጽሁፍ ክብር ይህንን ያህል ማዋረድ ይገባናል እንዴ? . ለሽሙጥና ግለሰቦችን ለመስደብ መፅሐፍ ከማሳተም ይልቅ አዝማሪ ቤት መክፈት አይሻልም ? እዚያም ቢሆን ግን ልክና ጨዋነትን ይጠይቃል፡፡እንደ እኔ እንደ እኔ የዚህ ዘመን አብዛኞቹ ጽሁፎች ቁም ነገር አዘል የማይሆኑት ካለማንበብ የተነሳ ነው፡፡ ምንም ሲጠፋ ከስድብ ውጪ በአፋችንም ሆነ በብዕራችን አይመጣም፡፡ ያልዘሩት አይታጨድምና! ብናነብ ግን የስነ ጽሁፍም ክብር ይገባን ነበር፡፡ ሚዛናዊነትን እንለምዳለን፤ ከመሳደብ ይልቅ ወደ መወያየት እንመጣለን፡፡ ትውልድን ላለማበላሸት ሃላፊነት ይሰማናል፡፡ ትውልድ ከሳንቲም ሽቀላ እንደሚበልጥ እንረዳለን፡፡ ሃገር መውደድና ለሃገር መታገል ትውልድን በጥላቻና በቂም ውስጥ እየዘፈቁ አይደለም፡፡ ለሆድ ሳይሆን በእውነት ለወገን በመቆርቆር ነው፡፡ አርቆ አሳቢ በመሆን! ብርን ብቻ መውደድ የቅርብ ቅዠት እንጂ የሃገር ህልም ሊሆን አይገባም፡፡ ቂምና ጥላቻን መዝራትም በሽታ ነው፡፡ ፈውስ የሚመጣው በቂም አይደለም፤ እውነትን በፍቅር በማስተላለፍ ነው፡፡

ሃገራችን በብዙ መልኩ ጥንካሬዎችዋን እያጣች የመጣች ይመስላል፡፡ ምናልባት ዓለማችንም ማለት ይቻላል፡፡ ሙዚቃው ለብለብ፣ ጽሁፉ ለብለብ፣ ምግቡ ለብለብ፣ ፖለቲካው ለብለብ እየሆነ ነው፡፡ የሃገራችንን ሁለንተና መለወጥ ያለብን እኛ ነን ብዬ አምናለሁ፡፡ እንግዲህ ያያችኋት ናት ሃገራችን - በጥበቡ ሰፈር፡፡ የገጣሚ ነቢይ መኮንንን “ሃገርህ ናት በቃ!” የምትል ግጥም አንብቡና ራሳችሁን ፈትሹ፡፡ ይቺው ናት ኢትዮጵያ ሃገርህ ናት በቃ! በዚች ንፍቀ-ክበብ፣ አይምሽ እንጂ መሽቶ፣ማታው ከጠረቃ የነቃም አይተኛ የተኛም አይነቃ፡፡ ይቺው ናት ዓለምህ፣ ብቻዋን የተኛች ከዓለም ተደብቃ!! አኪሯ ቀዝቅዞ፡- “ያንቀላፋች ውቢት” ያንተው የክት ዕቃ! ምን ትሆን እንግዲህ ሀገርህ ናት እሷ! ልቧን አታውልቃት አትጨቅጭቃት በቃ፣ አብረህ አንቀላፋ ወይ አብረሃት ንቃ!! ሁሉንም አወራን ባንል ትንሽ ነካካን፤ገናም ወደ ፊት እናወራለን፤ግን ሃገራችንን የምንሰራት እኛ ነን፤ማንም አይመጣልንም፡፡ ሽቀላ ብቻ አይደለም፤ ሃላፊነትም ሊሰማን ይገባል፡፡ በተለይ ጋዜጠኞቻችን እባካችሁ ክፉና ደግ ለመለየት እንኳ አንብቡ፡፡ ማንበብ ሙሉ ሰው ያደርጋል፡፡

Saturday, 06 April 2013 14:27

ቢራቢሮ

ቢራቢሮ እንደ ደብተር ተከፍታ ደረቷን ለጧት ፀሀይ ሰጥታለች፡፡ ደስ ማለቱ! የጧት ፀሀይ ሙቀቱ! ሽው ብሎ በላይዋ ላይ አለፈ - አስደንጋጭ የድምቢጥ ጥላ ክንፏ ዝግት! ጸጥ! ከነድንቢጥ ሆነ ከሌሎቹ የሞት መላእክት ራሷን የምትከላከልበት አንድም መሳሪያ የላት፡፡ ወላ ጥርስ - ወላ ቀንድ - ወላ መርዝ - ምንም! ምክር ፍለጋ ዶክተር አሊ ዘንድ ሄደች፡፡ ዶክተር ኤሊ ጥንት ከነቢዩ ኤልያስ ጋር ነበሩ፡፡ የመፃህፍትና የአበው ጥበብ በድንጋይ ልብሳቸው ሙሉ ተጽፏል እየተባለ ይነገርላቸዋል፡፡ “አበባን የፈጠርክ ፈጣሪ! አቤት አፈጣጠሩን ስታውቅበት! ኧረ ተመስገን!” እያለች ቢራቢሮ አበባዋ ላይ አረፈች፡፡ ወለላውን ልትጠጣ ብትሞክር ታድያ፣ በየት በኩል? ጥርሶቿ - እንዲያ በጥንቃቄ የመረጠቻቸውና እንዲያ ስትመካባቸው የቆየች ጥርሶቿ፣ አላስጠጣ አሏት፡፡

ይባስ ብለው ደሞ ያችን የጠራቻትን አበባ ቦጫጨቋት እነዚያ ባይተዋር ጥርሶች! ቅፅበታዊ ውስጣዊ ፀጥታ … ክንፏ ፀጥ እርጥ እስኪል ድረስ … “እንግዲያውስ ጥርስ ምን ሊያደርግልኝ ኖሯል? የኔ ምግብ እንደሆነ አይታኘክ፡፡ ለሳቅ ለፈገግታ እንደሆነ፣ የኔ ሳቅ ፈገግታዬ ክንፌና በረራዬ ውስጥ ያበራሉ፡፡ ሌላው ትርፍ ሸክም!” አለችና፣ እነዚያን የሾሉ ሹላሹል ጥርሶች ወድያ አሽቀንጥራ ጣለቻቸው (እዝጌርን ስትጐበኝ በስውር ሲሰልላት የነበረው ዲያብሎስ እንኳ ወደ ገሀነብ መቀመቅ ያን ያህል አልተወረወረም!) ከአበባዋ ወለላዋን ጠጣችና ጉዞዋን ስትቀጥል “ሆ! ኧረ‘ንኳንም ጥርስ አልፈጠረልኝ!” አለች፡፡

በሚቀጥለው ምእራፍ (ማለቴ በረራ) ቢራቢሮ ሲሾል የኖረ ሹል ጦሯን ወደ ሰማይ አሾለች አመቻቸችና፣ ክንፎቿን እስከ ጫፍ ዘርግታ ደረቷን ለፀሀይ ሰጥታ ስታበቃ “እነሆ በረከት! እነሆ ቢራቢሮ ለምሳ!” አለች፣ በክንፎቿ ክፍት ክድን የቢራቢሮ ሳቅ እየሳቀች፡፡ ሽው! ብሎ ወረደ - ለቢራቢሮ ሞትን የጫነ ድምቢጥ! ከሰማይ ያመጣችው ጦር ጥልቅ ሲልበት፣ ከህመሙ ይልቅ መገረሙ፣ መደንገጡ ብሶበት እዚያው ክንችር አለ፡፡ “አይ አቶ ድምቢጥ! ለካ የተጫንከው የኔን ሳይሆን የራስክን ሞት ኖሯል! ተመስገን!” እያለች ቢራቢሮ ሆዬ፣ ጦሩን ከድምቢጥየው ሬሳ ላይ ለመንቀል ብትሞክር ብትፍጨረጨር፣ እሷ ትቦጨቅ እንደሆነ እንጂ ጦሩ የማይነቃነቅ ሆነ፡፡ ደሞስ የደሙ ክርፋት! “እንግዲያውስ ጦር ምን ሊያደርግልኝ ኖሯል? ገድያቸው እንዲህ ከሚገሙኝ፣ እንዲህ እንደ ሰይጣን ፈስ ከሚከረፉኝ፣ ብቅ ሲሉ ክንፌን እጥፍ አድርጌ አልሰወርባቸውም? ይሻለኛልም ይቀለኛልም አለችና ጦሩን እዚያው ለድምቢጡ “ማስታወሻ ይሁንህ፣ ትቼልሀለሁ” እያለች ወደ ሰፈሯ ሄደች (ማለቴ በረረች)

 ሌላ የቢራቢሮ ምእራፍ (ማለቴ በረራ) እነሆ፡- ውድቅት ነው፡፡ ፍጡራን እንደየ ፍጥርጥራቸው በየፊናቸው ሲመገቡ አርፍደው፣ እንደአይነታቸው ውሀ ቸውን ጠጥተው፣ በየስፍራቸው እፎይ ብለው በማረፍም በማንቀላፋትም ላይ ናቸው፡፡ ይህን ጊዜ ቢራቢሮ አበባ ላይ ተመቻቸችና እዝጌር የሰጣትን፣ ከአንበሳ ጩኸት ሰባት ጊዜ ጐልቶ የሚጮኸውን አዲስየውን ጩኸቷን ለቀቀችው! ፍጡራን ከመበርገግ የባሰ በረገጉ፣ ብዙ ሯጮች ወለም አላቸው፣ በርካታ በራሪዎች ክንፋቸውን ቅርንጫፍ አቆሰላቸው፡፡ ፍጡር ሁሉ በየበረገገበት እንደየፍጥርጥሩ አደፈጠ፡፡ ብዙ ብዙ ቆይቶ በየፊናው አደጋውን ለማየት እዚህም እዚያም ተገላመጠ፡፡ ማንም የለም፡፡ ቀስ በቀስ ወደየስፍራቸው ተመለሱ፡፡ “እኔ ብቻ ሳልበረግግ” አለች ቢራቢሮ “እሱን ተይው! ያልበረገገ የለም” አሉዋት “ከኔ በስተቀር” “ኧረ ባክሽ? አሁንስ አንጎልሽም እንደ በረራሽ አበደ'ንዴ? አንበሳ ራሱ በርግጓል እንኳን አንቺ” “ሸረሪት ትጠየቅ” አለችና ቢራቢሮ የውልብልብ እየበረረች ሄደች … … እንግዲህ ሸረሪት ስትበረግግ መብረር ወይ መሮጥ ሳይሆን፣ ጥልቅ! ድብቅ! ሽፍን! ነው በዚያ በድርዋ - የምግብ ማግኛ መሳሪያዋ - ልብሷ - ቤትዋ - እንቁላል መጣያዋ - በጥበቧ ከገዛ ውስጧ የፈጠረችው ድርዋ፡፡ የምን ከንቱ ልፋት? ጥበቡን ሰጥቷታል፡፡

እና ከተሸሸገችበት ቀስ ብላ ብቅ ብትል፣ ቢራቢሮ ሆዬ አበባዋ ዙሪያ እየበረረች፣ ራሷን በራሷ እያባረረች በሳቅ ትንከተከታለች - የክንፍ ሳቅ “በረራሽ የእብድ መሆኑን አይቻለሁ” አለቻት ሸረሪት፡፡ ግን ፍጥረትን በሙሉ የሚያስበረግግ ጩኸት ሲያስቅሽ ሰባቴ ነው ያበድሽው፣ አንዴም አይደለ” “ያላስበረገገኝ ምክንያቱ የጮህኩት እኔ ራሴ ስለሆንኩ ነው’ኮ!” አለቻት - ቀለማት ክንፎቿን እያክነፈነፈች፡፡ “እየባሰብሽ ሄደ፡፡ አሁንማ ሰባ ጊዜ ሰባት አበድሽ!” ቢራቢሮ በረራዋን ትታ አበባዋ ላይ ቆመች - ተቀመጠች - ተሰየመችና፡- “አንቺ ተአምራዊ ድር ሊኖርሽ ከቻለ፣ እኔ ሃያል - መርእድ - መደንግጽ ጩኸት ሊኖረኝ ለምን አይችልም? ወይስ የተፈጥሮን ምስጢር ሁሉ ታውቂዋለሽ?” ሸረሪት ብዙ ስለማትንቀሳቀስ በጥሞና ለማሰብ ጊዜ አላት፡፡ ያውም ከድርዋ እኩል ተአምር የሆኑ ሀሳቦች፡፡

እርጋታ አለ ሸረሪት ቤት (ማለቴ ድር) ተረታችን ውስጥ፣ የመነኑት ባህታውያን እርጋታን ለመማር ወደ ሸረሪት ያተኩራሉ፣ ለሰባት ሙሉ ሰአት! (ያሬድ ማህሌታይን ሰባት አመት እናስታውሳለን) ስለዚህ ሸረሪት በእርጋታ “አሳምኚኝ” አለቻት ቢራቢሮን፤ “አዳሜ ፍጡሬ ከብርገጋዋ ተመልሳ በየስርፋዋ ታርፋለች፣ እማደል? ያን ጊዜ ትኩር ብለሽ እዪኝ፡፡ እጮሀለሁ፣ ይበረግጋሉ፡፡ አንቺ ግን ስጮህ እያየሽኝ ስለሚሆን አትደነግጪም” እንደተባባሉት ፍጡር ሁሉ እንደየድፍረትዋ፣ በየተራዋ በየስርፋዋ ተመልሳ አረፈች፡፡ ቢራቢሮ ለምናልባቱ ሸረሪትን ለማስጠንቀቅ ጥቂት በራረረች … አበባዋ ላይ አረፈች … እና ድምፁን … ጩኸቱን … ከፈጣሪ ቤት ያመጣችውን (እና፣ እብድም ይጠነቀቃልና፣ በጥንቃቄ የክንፏን ቀለም አስመስላ ክንፉ ላይ ለጥፋ ደብቃው የነበረውን ጩኸት) አነሳችና፡- አንድ ጊዜ ስትጮኸው ጊዜ፣ ፍጡሬ አዳሜ እንደ ቅድሙ አልበረገገላችሁም!? ቢራቢሮ እየበረረች ባበባዋ ዙሪያ በክንፏ ስትስቅ … ስትስቅ … ስትስቅ … “እሽ! እስቲ ዝም በይ አንዴ” አለቻት ሸረሪት “ሳይመለሱ ስሚኝ፣ ሲመለሱ ምንም እንደማናውቅ እናስመስል፡፡

በኋላ በየስርፋቸው ጩኸትሽን ስጪኝና አንዴ ልጩኸው” “እኔ ገና አልጠገብኩትማ!” “ተይ ተይ ተይ! አንዴ ብቻ? እሺ እንለዋወጥ፡፡ ያንቺን ጩኸት ላንዴ ብቻ ስጪኝ፣ የኔን ድር ጥበብ አስተምርሻለሁ፡፡ አቤት አንዴ ብትወዘውዢ! በኔ ድር! ሸሪሪት በሆንኩ! ትያለሽ፡፡” “እሺ” አለቻትና ተለዋወጡ፡፡ ቢራቢሮ በሀር ክር ጥቂት ከተወዛወዘች በኋላ ሰለቻትና “እንቺ ድርሽን፡፡ እኔ መሄዴ ነው” አለቻት “አንዴ’ንኳ ሳልጮህባቸው? ያውም እሺ ብለሽኝ?” “ኧረ አስር ጊዜ ጩሂ ተፈለግሽ! ጩኸቱን መርቄልሻለሁ” “ገና አልጠገብኩትም አላልሽም?” “አሁን ጠገብኩታ” አለችና ቢራቢሮ፣ የውልብልብ እየበረረች ሄደች “ደሞ ጩኸት ምን ያደርግልኛል?” እያለች ለራሷ “ትርፉ ሸክም!” ሸረሪትም “ቢራቢሮን ያሳበድክ ተመስገን!” እያለች ጩኸቱን ለእንስሳቱ እያከራየች እጅጉን ከበረች፡፡ ምን መክበር ብቻ? ሚሊዬነር ሆነች፡፡ ለፈጣሪ ምን ይሳነዋል? እያለች

“ለልጆቻችን ደህንነት ለማይጨነቁ ልበቢሶች ነው የሰራሁት” ካናዳዊው ኮሜዲያን ጂም ኬሪ የጦር መሳርያ የመታጠቅ መብትን ለመቃወም “ኮልድ ዴድ ሃንድ” የተሰኘ የሙዚቃ ቪድዮ በመስራት እንዳሰራጨ ተገለፀ፡፡ “ፈኒ ኦር ዳይ” በተባለ ድረገፅ የተለቀቀውን ይሄን ክሊፕ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሰው እንደተመለከተው የዘገበው ፎክስ ኒውስ፤ በኮሜዲያኑ ላይም ከፍተኛ ትችት እንደቀረበበት ጠቁሟል፡፡ ጂም ኬሪ ከአራት ዓመት በፊት ህይወቱ ያለፈውን የቀድሞ ተዋናይ እና የ“ናሽናል ራይፍልስ አሶሴሽን” ፕሬዝዳንት የነበረውን ቻርልስ ሄስተን ገፀባህርይ በመላበስ በካንትሪ ስልት ሙዚቃውን ተጫውቷል፡፡ በክሊፑ ላይ ጆን ሌነን፤ ማህተመ ጋንዲ እና አብርሃም ሊንከልንም ተተውነዋል፡፡

እስከ 10 ሚሊዮን የሚደርሱ አድናቂዎቹ በሚከታተሉት የትዊተር ማስታወሻው ላይ ጂም ኬሪ በፃፈው መልእክት፤ የሙዚቃ ቪድዮውን ለልጆቻችን ደህንነት ለማይጨነቁ ልበቢሶች ነው የሰራሁት ብሏል፡፡ በአሜሪካ ጦር መሳርያ የመታጠቅ መብት እንዲታገድ መጠነ ሰፊ ቅስቀሳ ሲካሄድ ቢሰነብትም ጦር መሳርያ የመታጠቅ መብትን የሚከለክል ህግ እንዲወጣ የሚደረገው ጥረት ስኬታማ መሆኑ ያጠራጥራል እየተባለ ነው፡፡ የኒውዮርክ ከንቲባ ማይክል ብሉምበርግ እስከ 12 ሚሊዮን ዶላር በጀት ይዘው የፀረ ጦር መሳርያ እንቅስቃሴ እያካሄዱ መሆኑን የዘገበው ብሉምበርግ ኒውስ ፤ በተቃራኒው በአሜሪካ መንግስት ከፍተኛ ተፅእኖ ያላቸው 15 ዴሞክራት እና ሪፐብሊካን ሴናተሮች የጦር መሳርያ የመታጠቅ መብትን ለመከልከል የተያዘውን ዘመቻ በይፋ እየተቃወሙ እንደሆነ አመልክቷል፡፡ ከ32 በላይ ፊልሞችን የሰራውና በመላው አለም እስከ 2.4 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ ገቢ ያስገባው ኮሜዲያን ጂም ኬሪ ፤ ቢያንስ 12 ያህል ፊልሞቹ ከ100 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ እንዳስገኙለት ይታወቃል፡፡

የብሪታኒያ ተዋናዮች በሆሊውድ ፊልም ሰሪዎች ተመራጭ እና ተፈላጊ እየሆኑ መምጣታቸውን ዘ ሆሊውድ ሪፖርተር አስታወቀ፡፡ በማራኪ የእንግሊዘኛ ቋንቋ አነጋገር፤ በምርጥ የትወና ብቃታቸው፤እንዲሁም በሚጠይቁት ተመጣጣኝ ክፍያ የእንግሊዝ ተዋናዮች ተመራጭ ሆነዋል ተብሏል፡፡ በበርካታ የሆሊውድ ፊልሞች መሪ ተዋናይነት በመስራት እና በመልመል አሜሪካውያኑን ከገበያ እያስወጡ እንደሆነም ዘ ሆሊውድ ሪፖርተር ዘግቧል፡፡

የእንግሊዝ ምርጥ የትወና ብቃት በሲኒማ ብቻ ሳይሆን በቲቪ ተከታታይ ፊልሞችም እየታየ ሲሆን በአሜሪካ የቴሌቭዥን ጣቢያዎች በአሜሪካውያን ህይወት ላይ የሚያጠነጥኑ ፊልሞች ላይ ሳይቀሩ እንግሊዛውያኑ በብዛት እየተወኑ ነው፡፡ የታላቋ ብሪታኒያ የፊልም ኢንዱስትሪ 100ኛ ዓመት ክብረ በዓል ከወር በኋላ ንግስት ኤልዛቤት በሚገኙበት እንደሚከበር የገለፀው ዘጋርድያን፤ በዚሁ ስነስርዓት ላይ በሆሊውድ ከፍተኛ ተቀባይነት ያገኙ የብሪታኒያ ምርጥ ተዋናዮች ይመሰገናሉ ብሏል፡፡

ድሮ ድሮ በሆሊውድ ፊልሞች የመጥፎ ገፀባህርያት ሚና ይሰጣቸው የነበሩ የብሪታኒያ ተዋናዮች፤ ከቅርብ አመታት ወዲህ ግን በከፍተኛ በጀት በተሰሩ፤ ታሪካዊ ይዘት ባላቸው እና በሱፐር ሂሮ ፊልሞች ላይ መተወን ይዘዋል፡፡ በሆሊውድ የእንግሊዞቹ ዋና ተፎካካሪዎቻቸው አውስትራሊያውያን ብቻ እንደሆኑም ታውቋል፡፡ አንቶኒ ሆፕኪንስ፤ ማይክል ኬን፤ ጋሪ ኦልድማን፤ ሲን ኮነሪ፤ሁውጅ ግራንት፤ራልፍ ፊነስ በሆሊውድ በግንባር ቀደምነት የሚጠቀሱ የእንግሊዝ ተዋናዮች ናቸው፡፡

በ“ሊንከለን” ፊልም ላይ የተወነው እንግሊዛዊው የፊልም ባለሙያ ዳንኤል ዴይ ሊውስ ለሶስተኛ ጊዜ በምርጥ ተዋናይነት የዘንድሮን ኦስካር በመውሰድ ሪከርድ ያስመዘገበ ሲሆን ባለፉት አምስት ዓመታት ከአምስት በላይ የብሪታኒያ ተዋናዮች የኦስካር ሽልማቶችን እንደወሰዱ ይታወቃል፡፡ 2013 ከገባ ወዲህ ክርስትያን ቤል፤ጃሬድ ሃሪስ፤ ዳንኤል ዴይ ሊውስ፤ ኢድሪስ ኤባ እና ሌሎች እንግሊዛውያን ተዋናዮች በምርጥ የሆሊውድ ፊልሞች ላይ በመሪ ተዋናይነት በመተወን ተወዳዳሪ አልተገኘላቸውም፡፡

የሊል ዋይኔ አዲስ አልበም ‹‹አይ አም ኖት ኤ ሂውማን ቢንግ 2›› በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ለገበያ የቀረበ ሲሆን ሽያጩ እንደሚደራለት ከወዲሁ ተገምቷል፡፡ ከሳምንት በፊት ሊል ዋይኔ ከድንገተኛ የልብ ህመም ጋር በተገናኘ በገጠመው የጤና እክል ከሞት አፋፍ እንደተረፈ ተዘግቧል፡፡ በማህበረሰብ ድረገፆች አነጋጋሪ በመሆን በአንድ ሳምንት ውስጥ ከቀድሞው የ19ኛ ደረጃ ወደ ሁለተኛ ደረጃ የተመነደገው ራፐሩ፤ አጋጣሚው ለአዲሱ አልበሙ ጥሩ ማሻሻጫ ይሆንለታል ተብሏል፡፡ ራፐሩ ከሚወስደው ሃይል ሰጭ መጠጥ ጋር በተያያዘ ለህይወቱ የሚያሳስብ አደገኛ ደረጃ ላይ ደርሶ እንደነበረ ያወሱት ዘገባዎች ፤ ሆስፒታል ገብቶ በተደረገለት ከፍተኛ የህክምና ክትትል ህይወቱ እንደተረፈ ጠቁመዋል፡፡ ሊል ዋይኔ የገጠመው የጤና እክል ከጭንቀት ጋር በተያያዘ የተፈጠረ እንጅ በአደገኛ እፅ ተጠቃሚነት አለመሆኑን ያስተባበለው የአሳታሚው “ካሽ መኒ” ስራ አስኪያጅ ፤ በቂ እረፍት በመውሰድና ራሱን በማዝናናት ጤንነቱ እንደሚመለስለት ተናግሯል፡፡

ከ2013 ምርጥ አልበሞች አንዱ እንደሚሆን ተስፋ የተጣለበት የሊል ዋይኔ አዲስ አልበም በከፍተኛ ጉጉት ሲጠበቅ እንደቆየ የዘገበው ሮሊንግ ስቶን መፅሄት፤ በአልበሙ ላይ ኒኪ ማንጅ፤ ድሬክ፤ ቢግ ሲን፤ ገን ፕሌይ እና ሌሎች ራፐሮች በአጃቢነት እንደሰሩ አመልክቷል፡፡ የአልበሙን ሽፋን ምስል የሰራለት የሂፖፕ ሙዚቀኛው ካናዬ ዌስት እንደሆነ የገለፀው መፅሄቱ ፤ ሊል ዋይኔ የዓለም ምርጥ ራፐር መሆኑን ካናዬ መመስከሩንም ጨምሮ አስታውቋል፡፡ ራፐሩ ከሁለት ዓመት በፊት ‹‹አይ አም ኖት ኤ ሂውማን ቢንግ›› በሚል ስያሜ የመጀመርያውን የአልበሙን ክፍል ለገበያ እንዳበቃ የሚታወስ ነው፡፡ ሊል ዋይኔ ከአዲሱ አልበሙ ‹‹አይ አም ኖት ኤ ሂውማን ቢንግ 2›› በኋላ አጠቃላይ የስራዎቹን ብዛት 11 ያደረሰ ሲሆን በሙዚቃ ህይወቱ 95 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ሃብት ማፍራቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡