Administrator

Administrator

Saturday, 04 May 2013 11:37

ኢትዮ-ቴሌኮምና ችግሮቹ

“የስልክ ጥራት ችግር ከእድገቱ ጋር የመጣ ነው”

የቴሌኮምኒኬሽን አገልግሎት የጥራት መጓደል ቀድሞም የነበረው ጉዳይ ቢሆንም ከቅርብ ጊዜያት በተለይም በሣምንታት እድሜ ከሚቆጠር ጊዜ ወዲህ ዘርፈ ብዙ ችግሮች እየተስተዋሉበት ነው። በሞባይል እየተነጋገሩ አገልግሎት በድንገት ተቋርጦ አየር ላይ መቅረት፣ የድምፅ በጥራት አለመሠማት፣ በአንድ አካባቢ ካለ ወዳጅ ጋር እንኳ መገናኘት አዳጋች እየሆነ ነው፡፡ በተመሣሣይ ዘመኑ የፈቀደውን በይነ መረብ (ኢንተርኔት) አገልግሎት ለመጠቀም ብንሞክርም ከመንቀራፈፉም በላይ እንደ ሞባይል ንግግሩ እሡም የሚቆራረጥበት ጊዜ ይበረክታል፡፡ የመደበኛ (መስመር) ስልክም ቢሆን ሲበላሽ ለማስጠገን የገነት መግቢያ ያህል መትጋትን የሚጠይቅ ከሆነ ሠነባብቷል፡፡ ታዲያ የጉዳዩ ዋነኛ ባለቤት የሆነው ኢትዮ ቴሌኮም እነዚህ መሠረታዊ የጥራት ችግሮች እንዴት አጋጠሙት፣ በቀጣይስ በምን አግባብ ሊፈታቸዉ አሠበ ስንል ጠይቀናል፡፡ በኢትዮ - ቴሌኮም የኮርፖሬት ኮሚኒኬሽን ሃላፊው አቶ አብዱራሂም አህመድም ለጥያቄያችን ምላሽ ለመስጠት በርካታ ቀናት ያህል በተለዋዋጭ ቀጠሮዎች ቢያቆዩንም ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር በነበራቸው ቆይታ በተነሡት ርዕሠ ጉዳዮች ዙሪያ ተነጋግረዋል፡፡

የተንቀሣቃሽ ስልክ አገልግሎት የኔትወርክ መቆራረጥ፣ የድምፅ ጥራት መቀነስ የመሣሠሉት ችግሮች በስፋት እየተስተዋሉ ነው፡፡ ኢትዮ ቴሌኮም እነዚህን ለማስተካከል ምን እርምጃ እየወሠደ ነው? የተንቀሣቃሽ ስልክ ኔትወርክ እና መቆራረጥ ችግሮች በዋናነት በሁለት ልንከፍላቸው እንችላለን። የመጀመሪያው አዲስ አበባ ላይ የሚታዩት ናቸው፡፡ አዲስ አበባ ደግሞ ተለይተው የሚታወቁ ቦታዎች አሉ፡፡ የኖክያ አካባቢ የሚባል አለ፣ ከአስኮ ጀምሮ በኮልፌ ቀራኒዮ በአስራ ስምንት ማዞሪያ፣ በሉካንዳ፣ አለምገና፣ አየር ጤና፣ መካኒሣ፣ ካራቆሬ፣ ቄራ እና እስከ ሃና ማርያም የሚደርስ፡፡ ይሄ ከ10 አመት በፊት የተተከለ ነው፡፡ እዚህ አካባቢ ያለው ተጠቃሚ አገልግሎቱን በአግባቡ እያገኘ አይደለም። ይሄ የሚታወቅ ነው፡፡ መፍትሄው ሁለት ነው። አንደኛ ጊዜያዊ መፍትሄ አለ፤ ሁለተኛው ቋሚ/ዘላቂ የሚባለው ነው፡፡ ጊዜያዊ መፍትሄ ስንል በዚህ በጠቀስኳቸው ቦታዎች ያለውን ኔትወርክ የማሣደግ ስራ ነው፡፡ ዘላቂው ስራ ደግሞ ይሄንን ሙሉ ለሙሉ በአዲስ የመቀየሩ ስራ ነው፡፡ አሁን ጊዜያዊ መፍትሄው እየተሠራ እያለ ሙሉ በሙሉ የመቀየሩ ስራ ግን በጥቂት ወራት ውስጥ ተሠርቶ ይጠናቀቃል ማለት ነው፡፡

በዋነኛነት አዲስ አበባ በተቋሙም እንደሚታወቀው የአገልግሎት ጥራት ችግር አለ፡፡ በአካባቢው ያለው ከአምስት አመት በፊት የተዘረጋ ኔትወርክ ነው፡፡ ለምሣሌ እንደ ጀሞ፣ ለቡ ያሉትን ብንወስድ መሠረተ ልማት ከመዘርጋቱ በፊት በዚያ አካባቢ የነበረው ነዋሪ በጣም ትንሽ ነው፡፡ አሁን ግን ጀሞን ብቻ ብንወስድ ከ40ሺህ በላይ ነዋሪ ያለበት ነው፡፡ እና ይሄንን በየጊዜው የማሣደግ ስራ እንዳለ ሆኖ የመቀየርና የማሣደግ ስራ ይሠራል፡፡ እዚህ አካባቢ ተጠቃሚው አገልግሎቱን በተገቢው መልኩ እያገኘ አይደለም፡፡ ሁለተኛ አዲስ አበባን አጠቃላይ ስንወስድ ከኔትወርክ ጥራቱ ችግር ጋር የምናነሣው የህንፃዎችን ማደግ ነው፡፡ ህንፃዎች ሲያድጉ የቴሌኮም አንቴናዎች በአንፃሩ የተተከሉት መሬት ላይ ነው፡፡ አሁን ኔትወርኩን ለማሣደግ አንቴናዎች ህንፃዎች ላይ መተከል አለባቸው፡፡ ግን ይህን ለማድረግ እስከ አሁን ፈቃደኛ የሆነ ባለ ህንፃ የለም፡፡ ነገር ግን በህጉ የተቀመጠ አለ፡፡

የትም ቦታ በአግባቡ የቴሌኮም መሠረተ ልማት የመዘርጋት ግዴታ አለ። ይህም ሲባል ተገቢውን ክፍያ በመክፈል ነው፤ ሌላው ተደጋጋሚ የኤሌክትሪክ ሃይል መቆራረጥ እያጋጠመን ነው። እያንዳንዱ አንቴና በኤሌክትሪክ ሃይል ነው የሚሠራው፡፡ የኤሌክትሪክ ሃይል ሲቋረጥ ችግሩ ይፈጠራል፡፡ ሌላው የተጠቃሚው ቁጥር መጨመር ነው፡፡ በ2002 ያለው 6.7 ሚሊዮን ነበር አሁን ያለው 22 ሚሊዮን ተጠቃሚ ነው። በአጠቃላይ ጥራቱ ላይ የሚስተዋሉት ችግሮች እነዚህ ሲሆኑ ከእድገቱ ጋር የመጡ ናቸው፡፡ መቼ ነው ታዲያ የሚስተካከለው? በጥቂት ወራት ውስጥ፡፡ አሁን ይሄንን መሠረተ ልማት ለመቀየር የሚያስችል ስራ እየሠራን ነው፡፡ ይሄ ስራ በቅርቡ ይጠናቀቃል፡፡ የቅድሚያ ቅድሚያ ተሠጥቶት የሚሠራው ዝርጋታውን የማቀላጠፍ ስራ ነው፡፡ የሃይል መቆራረጡን በተመለከተ ለእያንዳንዱ አንቴና ብቻ ሣይሆን አቀባባይ ለምንላቸው ጄኔሬተር የማቅረብ ስራ እየሠራን ነው፡፡

ከህንፃዎች ጋር ያለውንም ከባለ ህንፃዎች ጋር በመነጋገር ወደ ስራው በመግባት ነው ችግሩ የሚፈታው፡፡ የኢንተርኔቱ መቆራረጥስ ከምን ጋር ነው የሚያያዘው? የኢንተርኔቱን መቆራረጥ በሁለት መልኩ ልናየው እንችላለን፡፡ የመጀመሪያው የፋይበር ኦፕቲክ ገመድ መቆረጥ ጋር እናያይዘዋለን፡፡ የፋይበር ኦፕቲክስ ፋይበር አሁን በሃገራችን ከ12 ሺህ ኪሎ ሜትር በላይ ተዘርግቷል፡፡ በ45 አቅጣጫዎች ማለት ነው፡፡ ይሄ ዋነኛ አላማው የሃገር ውስጡን ግንኙነት ማቀላጠፍ ነው፡፡ ለአለማቀፍ ግንኙነት የምንጠቀምባቸው ደግሞ ሶስት አቅጣጫዎች አሉ፡፡ ከአዲስ አበባ - መተማ አድርጐ ፓርት ሱዳን የሚሄደው፣ ሁለተኛው ከአዲስ አበባ ጅቡቲ የሚሄደው፣ ሶስተኛው ከአዲስ አበባ በሃዋሣ አድርጐ ሞያሌ ሞንባሣ የሚደርሠው ነው፡፡

ይህ ፋይበር ኦፕቲክ እንግዲህ እየሠጠ ያለው አገልግሎት ሁለት ነው፡፡ አንደኛ የሃገር ውስጡን ትራፊክ ይሸከማል። ሁለተኛ አለማቀፍ ግንኙታችንንም ያከናውናል። ወደ ኢንተርኔት ስንመጣ ለኢንተርኔት ግንኙነት ከሣተላይት በተጨማሪ በእነዚህ ሶስቱ መስመሮች ነው ግንኙነታችን፡፡ እነዚህ ሶስቱም ወደ ባህር ሄደው በባህር ጠለቅ ኬብል አድርገው ጄዳ፣ ከዚያ ለንደን ደርሠው ነው የአለማቀፍ ግንኙነታችንን የሚያሳልጡ፡፡ እንግዲህ ፋይበር ኦፕቲክ ኬብል ተቆረጠ ማለት በድሮው ከሆነ አገልግሎት ይቋረጣል ማለት ነው፡፡ ለምሣሌ ከዚህ መተማ ያለው ደባርቅ ላይ ቢቋረጥ፣ አንደኛ የባህር ዳር አካባቢ ግንኙነት ይቋረጣል፡፡ ከዛ አልፎ በፖርት ሱዳን አድርጐ የሚሄደው ግንኙነታችንም ይቋረጣል፡፡ አሁን ግን እዚያ ደረጃ አይደለንም፤ በማይክሮዌቭ እንገናኛለን።

ሁለተኛ በቀለበት መልኩ የተዘረጋ ስለሆነ ደባርቅ ላይ ቢቋረጥ ባህር ዳርን በመቀሌ ወይም በደሴ አድርገን እናገኘዋለን፡፡ በዚህ መፍትሄ አገልግሎቱ አይቋረጥም ግን ጭነቱ በትክክል ወደሚሠራው ይመጣል፡፡ በዚህ ጊዜ የኢንተርኔት ግንኙነት በጣም ይጓተታል ማለት ነው፡፡ አንዱና ትልቁ ችግር እሡ ነው፡፡ ይህ በአለማቀፍ ደረጃም ያጋጥማል፡፡ አሁን እኛ በሶስት ባህር ጠለቅ ኬብል በምንገናኝበት ላይ በቅርቡ ያጋጠመ አለ፡፡ በሜዲትራኒያን አካባቢ ተቆርጦ ከሰባት ቀን በላይ አገልግሎት የመጨናነቅ ሁኔታ ነበር፡፡ ከ177 ሠአታት በላይ ተቋርጧል፡፡ ይሄ እንግዲህ ከእኛ አቅም ውጪ የሆነ ነው ማለት ነው። ይህ በሚቋረጥበት ጊዜ ተጠቃሚው በአግባቡ አገልግሎቱን አያገኝም ማለት ነው፡፡ ሁለተኛው በከተማ ውስጥ ተደጋጋሚ መብራት በሚቋረጥበት ጊዜ ማስተላለፊያ ሣጥኖች አሉ፤ ድሮ ኬብል ካቢኔት የምንላቸው ማለት ነው፡፡ ከ45 አመት በፊት ተተክለው የነበሩና በመዳብ የሚሠሩ ናቸው፡፡

እነዚያ አሁን ከአራት አመት በፊት ነው የተቀየሩት። እነዚያ የራሣቸው የአቅም ውስንነት ነበራቸው፡፡ አቅማቸው ውስን ስለነበረ በዋነኛነት የድምፅ አገልግሎት ብቻ ነበር የሚሠጡት፡፡ ከ600 ያነሠ መስመር ነበር የሚይዙት፡፡ አሁን ግን ሁሉም በፋይበር ተቀይረው የእስክሪፕቶ ቀፎ ስፋት መጠን ያለው ኬብል ከ10ሺህ በላይ መስመር የመያዝ አቅም አለው፡፡ እነዚህ ሁሉ በኤሌክትሪክ ነው የሚሠሩት። ተደጋጋሚ የሃይል መቆራረጥ በሚደርስበት ጊዜ አንደኛ አቅማቸው እየደከመ ነው የሚሄደው፡፡ ሃይል በሚቆራረጥበት ጊዜ ባትሪው አቅሙ እየደከመ ነው ይሄዳል፡፡ ሙሉ በሙሉ ሊቃጠልም ይችላል፡፡ ወደ መፍትሄው ስንመጣ፣ አንደኛ የፋይበር ኦፕቲክ መቆረጥን ለመታደግ በተለይ አለማቀፍ ግንኙነታችን ላይ ኢፒጂ ደብሊው የሚባል አለ በዚያ ነው እየዘረጋን ያለነው፡፡

ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ኮርፖሬሽን ጋር ስምምነት አድርገን ከፍተኛ የሃይል ጭነት በሚባለው የኤሌክትሪክ መስመር ላይ ነው ወደ ሞምባሣ እና ወደ ሌሎቹ አካባቢዎች የሚሄደውን መስመር እየዘረጋን ያለነው፡፡ ይህ ሲሆን በምንም መልክ ሊቆረጥ አይችልም፡፡ ከሦስት አመት በፊት በዓመት 34 የፋይበር ኦፕቲክ መቆረጥ ብቻ ነበር የሚደርሠው፡፡ አሁን ግን በወር ከ45 በላይ አንዳንዴም 60 ይደርሣል፡፡ ይሄ ማለት በአገልግሎት ጥራቱ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ አለው፡፡ ወደ ህጉ ከመጣን፣ አንዳንድ ሃገሮች ፋይበር ኦፕቲክ ለቆረጠ የሞት ቅጣት ፍርድን አስቀምጠዋል፡፡ በእነዚህ ሃገራት እንኳን ኬብል ቆርጦ አገልግሎት የሚያቋርጥ ቀርቶ በአጠገቡም የሚያልፍ የለም፡፡ በወር 45 ጊዜ የሚቆረጥበት ሃገር ከኢትዮጵያ በስተቀር የለም፡፡ አሁን እንደተቋም ሌላ መፍትሄ ብለን የያዝነው በአየር ሞገድ የሚሄድ ማይክሮዌቭ ማስተላለፊያ አለን፡፡

ይሄ በየትም በኩል ቢቆረጥ አገልግሎቱ አይቆምም፤ ነገር ግን መጨናነቅ ይፈጥራል፡፡ የኤሌክትሪክ መቆራረጥን እንደ ችግር ደጋግመው እያነሡልኝ ነው፡፡ ሁለቱ አካላት መ/ቤቶች ተነጋግራችሁ ችግሩን መፍታት አልተላችሁም ማለት ነው? በጋራ እየሠራን ነው፡፡ በተለይ በጣም መሠረታዊ የሚባሉ አገልግሎቶቻችን ላይ ከእነሡ ጋር እየሠራን ነው፡፡ እንደ ሃገር በሚደርሠው መቆራረጥ ነው እኛ ጀነሬተር፣ ባትሪ የመሣሠሉትን መፍትሄዎች የምንጠቀመው፡፡ ነገር ግን መሠረታዊ የሚባሉት ላይ ከእነሱ ጋር እየተመካከርን ነው፡፡ የመስመር ስልኮች በአብዛኛው አካባቢዎች ሲቋረጥ ደንበኞች ለመስሪያ ቤቱ ቢያመለክቱም መፍትሄ እንደማይሠጥ በርካቶች እንደስሞታ ያቀርባሉ፡፡ አገልግሎቱ የሚቆራረጥበት ምክንያት ምንድን ነው? ለምንድንስ ነው በፍጥነት ምላሽ የማይሠጠው?

በመሠረታዊነት ከመደበኛ የስልክ መስመር ጋር ተያይዘው የሚታዩ ችግሮች አሉ፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ በጣልያን ጊዜ የተዘረጋ የኮፐር ኬብል ነበር። አሁን እያጋጠመ ያለው መሠረታዊ ችግር ከተማዋ እያደገች ያለች ነች፡፡ ከመንገድ እና ከልማት ስራዎች ጋር በተያያዘ የኬብል መቆራረጥ ይከሠታል፡፡ ሁለተኛ ደግሞ የማይግሬሽን ስራም እየተሠራ ነው፤ ማለትም ድሮ ከነበረበት ወደ አዲሱ (ከመዳብ ወደ መልቲ ሠርቨር ኬብል ጌትዌይ) እየተሸጋገረ ነው፡፡ ከማዛወሩ ጋር ተያይዞ የሚታዩ ችግሮች አሉ፡፡ የአንዳንዶቹ ያለ መግባት፣ የመሣት የመሣሠሉ ችግሮች አሉ፡፡ ከጥገና ጋር ተያያዞ የተነሣው ማንኛውም ደንበኛ ብልሽት ሲያጋጥመው በስልክ ደውሎ ያስመዘግባል፡፡ ከዚያ ቲቲ ቁጥር (Travel ticket Number) ይሠጠዋል፡፡ ከተቀበሉ በኋላ በየዞኑ በየአካባቢው ላሉ አካባቢዎች ተላልፈው፣ እዚያ ያሉ ባለሙያዎች እንዲሠሩት ይደረጋል፡፡ ይሄ ሲባል ግን ችግር አያጋጥምም ማለት አይደለም፤ ያጋጥማል፡፡

ነገር ግን ችግር የደረሠባቸው ተጠቃሚዎች ወደ ተቋሙ ቀርበው በአካል ቢያመለክቱ መልካም ይሆናል፡፡ በአጠቃላይ ግን የተንቀሣቃሽ፣ የኢንተርኔት እንዲሁም የመደበኛ ስልክን በተመለከተ ተቋሙ ጥራትን መሠረት አድርጐ ሊሠራ እየተንቀሣቀሠ ነው፡፡ ወደ 26 ፕሮጀክቶች ተቀርፀዋል፡፡ እስካሁን ትልቁ ትኩረት የነበረው መሰረተ ልማቱን የመዘርጋት ነበር፡፡ አሁን ግን ወደ ጥናት መሄዱ ትኩረት ተደርጐበታል፡፡ በየሣምንቱ ይህን በተመለከተ ስራ አስፈፃሚው ተሠብስቦ ይገመግማል፡፡ በተለይ ከመደበኛ የመስመር ስልኮች ጋር የሚታዩ ችግሮች ይኖራሉ፡፡ በተቋሙም እነዚህ ችግሮች ይታወቃሉ፡፡ ግን ችግራቸው ለብዙ ጊዜ የዘለቀባቸው ወደ ተቋሙ ቢመጡ የማስተካከል እርምጃ ይወሠዳል፡፡ በአጠቃላይ ግን የተቋሙ ዋነኛ እቅድ በዚህ አመት መጨረሻ ላይ 40 ሚሊዮን የሞባይል ተጠቃሚ እንዲኖር ማድረግ ነው፡፡ አሁን 22 ሚሊዮን ነው ያለነው፡፡ አፈፃፀሙን ካየነው በ2003 እና በ2004 ከእቅዱ በላይ ነው ያሣካው። በሞባይል አገልግሎት አሁን ከአፍሪካ በ6ኛ ደረጃ ላይ ነው ያለነው፡፡ ከአራት ዓመት በፊት 13ኛ ነበርን፣ የዛሬ ሁለት ዓመት ደግሞ 9ኛ ሆንን፣ ዓምና 6ኛ ሆነናል፡፡ ኬንያን ቀድመን ማለት ነው፡፡

ከአፍሪካ እኛን የሚደቀድሙን ናይጄሪያ፣ ግብፅ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ሞሮኮ እና አልጄሪያ ናቸው፡፡ የአንድ ሃገር የቴሌኮም ልማት የሚለካው በሃገሪቱ ያለው የቴሌኮም ቁጥር ለህዝቡ ሲካፈል በሚገኘው ውጤት ነው፡፡ በዚህ ደረጃ እኛ ፔኔትሬሽን ሬታችን ወደ 28 በመቶ ደርሷል፡፡ ከ20 አመት በፊት 0.25 በመቶ ነበር አሁን 25 በመቶ ደርሠናል፡፡ በቀጣይ ሁለት አመት ደግሞ ከእጥፍ በላይ ለማድረስ ነው ጥረት የሚደረገው፡፡ ሠራተኞቻችሁ የሰዎችን የስልክ ጥሪ ልውውጥ ሚስጥር ለሰው ያሳያሉ ይባላል? ይህን ማድረግ ይቻላል? በመሠረቱ የኛ ተቋም የስልክ ንግግርን አይቀዳም። እኛ ያለን ተጠቃሚው የደወለበት (Call detail record) ዝርዝር ነው፡፡ አንድ ተጠቃሚ መቼ፣ በስንት ሰአት፣ የት ደወለ የሚለው ነው ያለን፡፡ ከዚህ ውጪ የመልዕክቱን ፍሬ ሃሳብ የሚመዘግብም መሣሪያ የለንም፡፡ በስልክ የተለያዩ ወንጀሎቹ ይሠራሉ፡፡ ለምሣሌ ዛቻ ሲፈፀም ፖሊስ በምርመራ ሲጠይቃችሁ ኮምፒውተር ውስጥ የለም፤ አልተመዘገበም ይባላል። ለምንድን ነው? ከዚህ ጋር በተያያዘ ማንኛውም ተጠቃሚ ዛቻ እና የመሳሰሉት ሲደርሱበት በመጀመሪያ ለፖሊስ ያሳውቃል፡፡ ፖሊስ በምን ስልክ ነው የደረሰብህ ይላል።

ከዚያም ወደ ተቋማችን መጥቶ ፖሊስ የሚጠይቀው አንደኛ በዚህ ቁጥር ላይ ያለው ማን ነው? ሁለተኛ ደግሞ ያደረገውን ልውውጥ ሪከርድ ነው፡፡ ይህ ሲሆን ነው አልተመዘገበም የሚባለው። አሁን ሲምካርድ እየተሸጠ ያለው በተለያዩ የግል አቅራቢዎች ነው። በመሠረታዊነት በደንቡ እያንዳንዱ ሲም ካርድ አከፋፋይ በሚሸጥበት ጊዜ የእያንዳንዱን ገዢ ሙሉ አድራሻ መያዝ አለበት፣ አድራሻ ሳይዝ ከሸጠ እሱ ነው ተጠያቂ፣ ያ አድራሻው ሳይያዝ የተሸጠለት ግለሰብ ወንጀል ቢሠራና ፖሊስ መረጃውን ቢጠይቅ እኛ ጋር ስለማይመዘገብ አድራሻው ኮምፒውተር ውስጥ የለም ማለት ነው፡፡ ይህን ተገንዝቦ ማንኛውም አከፋፋይ የሚሸጥለትን ሰው ሙሉ አድራሻ በሚገባ መያዝ አለበት፡፡ በሞባይል ለተጠቃሚዎች ከእናንተ ተቋም እና ከሌሎች የንግድ ድርጅቶች የሚላኩ አጭር መልዕክቶች የሰዎችን ፍላጐት የጠበቁ አይደሉም፣ የሰአት ገደብ ስለሌላቸውም ሌሊት ሳይቀር መልዕክቶቹ ይላካሉ ተጠቃሚውንም ይረብሻሉ፣ ተቋሙ ይሄን ነገር እንዴት ነው የሚያየው? እስካሁን ይሄንን አሠራር አቅጣጫ የሚያሳይ አዋጅ አልነበረም፤ አሁን ግን አዋጅ አለ፡፡ የብሮድካስት አዋጅ ላይ በትክክል ተቀምጧል፡፡

ወደ ስራ ሲገባ በቀጣይ እያንዳንዱ ተጠቃሚ አስቀድሞ ማስታወቂያ ትፈልጋለህ ወይ ተብሎ መጠየቅ ይኖርበታል፡፡ አዎ እፈልጋለሁ ብሎ ከላከ ይላክለታል፡፡ አልፈልግም ካለም አይላክለትም። ይህን ለመከታተል የብሮድካስት ባለስልጣንም አለ፤ ኢትዮቴሌኮምም ባለድርሻ ነው። በቀጣይ ወደተግባራዊ ስራው ለመግባት ባለድርሻ አካላቱ እየተወያዩበት ነው፡፡ መልዕክቶቻችሁ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ነው የሚተላለፉት፡፡ ምን ያህል ደንበኛ በአግባቡ ይረዳናል ብላችሁ ታስባላችሁ? በመሠረታዊነት እኛ ሀገር ያሉ ቀፎዎች አማርኛን የሚቀበሉ አይደሉም፡፡ አብዛኛው በእንግሊዝኛ ነው። በዚህ ደግሞ እኛም እየተቸገርን ነው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን የሃገር ውስጥ ቋንቋን ታሳቢ የሚያደርጉ እየመጡ ነው፡፡ በኛ ሃገር አሁን ባለው ከኢንተርኔት ከ80 በመቶ በላይ የመረጃ የምንቀዳው (Download) በሌላ ቋንቋ ነው፡፡ እኛ በሀገር ቤት ቋንቋ የምንጭነው መረጃ የለንም፡፡ እኛ ቢሆንልን በሁሉም ቋንቋዎች መላክ እንፈልጋለን፡፡ ነገር ግን ይሄን የሚያስተናግድ ቀፎ ተጠቃሚ ጋር የለም፡፡ አሁን ያሉት የሃገር ውስጥ ቋንቋ ቀፎዎች ከ1 በመቶ በታች ናቸው፡፡

እንዴት ሰነበታችሁሳ!

እንኳን ለብርሀነ ትንሳኤው በሰላም አደረሳችሁማ! ያው ‘ኔትወርክ’ እንደተለመደው በበዓል ሰሞን እንደልብ ስለማይሠራ ‘መልካም የትንሳኤ በዓል’ የሚል ‘ቴክስ ሜሴጅ’ ለሁሉም መላኬ ይመዝገብልኝማ! ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…አንዳንዴ ሳስበው ይሄ ‘ኔትወርክ’ የሚባል ነገር ልክ የሰው ባህሪይ ይዞ የሚያሾፍብን ይመስለኛል፡፡ ልክ ነዋ… አጠገብ ለአጠገብ ቆማችሁ ስትደዋወሉ… “ይቅርታ የደወሉላቸውን ደንበኛ አሁን ማግኘት አይችሉም…” ምናምን የሚል ነገር ስትሰሙ የምር አስቸጋሪ ነው፡፡ ነው…ወይስ ይሄ እንደ አንዳንድ ከማዳን ይልቅ በሽታ ያብሳሉ እንደሚባሉት ከውጪ የሚመጡ መድሀኒቶች ለእኛ የሚለቀቀው ቴክኖሎጂ ‘ከማዳን የሚያብስ ነው!’ ልክ ነዋ…ቴክኖሎጂ እንዲህ በተራቀቀበት ዘመን ጎን ለጎን ሆነን እንኳን “…ማግኘት አይችሉም…” ነገር ስንባል…አለ አይደል… የሰዉ አንሶን ቴክኖሎጂም ያሹፍብን ብንል አይበዛብንም! “ኸረ እባክሽ አንቺ ሴትዮ ጎን ለጎን ነው የቆመነው!” ምናምን ለማለት አስቸጋሪ ሆነብንና…አለ አይደል… እንዲሁ ‘የገበጣ ጠጠር’ ሆነን ቀረን፡፡

በቃ…የገበጣ ጠጠር ባንከባለሉት በኩል መንከባለል ነው እንጂ ‘ኮምፕሌይንት’ ‘ፔቲሽን’ ቅብጥርስዮ ምናምን ነገር የለማ! እናላችሁ… አጠገብ ለአጠገብ ሆነን እንኳን “የደወሉላቸውን ማግኘት አይችሉም…” አይነት ነገር እነዚህ አፍ፣ ጆሮዎችና ዓይኖቻቸውን እንደሸፈኑት ጦጣዎች ምስል እየሆንን ነው፡፡ የምንናገረው ነገር እንደየሰዉ አተረጓጎም ሆኖ ‘የተደወለላቸው አልገኝ’ እያሉ ችግር እየሆነ ነው፡፡ “…የደወሉላቸውን ደንበኛ አሁን ማግኘት አይችሉም…” በሁሉም ነገር እያየነው ነው፡፡ ለምሳሌ “አበበ በሶ በላ…” አለ አይደል…በቃ ጣጣ የለውም፣ “አበበ በሶ በላ…” ማለት ነው፡፡ በዚህ ዘመን ግን እያንዳንዳችን የየራሳችንን መዝገበ ቃላት ፈጠርንና ግንኙነታችን ሁሉ ‘የባቤል ግንብ’ ታሪክ አይነት እየሆነ ነው፡፡ የምር… ለምሳሌ አንዱ የእኔ ቢጤ “አበበ በሶ በላ…” የሚለውን የዓረፍተ ነገር አወቃቀር መማሪያ…“አበበ ካልጠፋ ምግብ ለምን በሶ እንዲበላ ተደረገ?” የሚል ሙግት ሊጀምር ይችላል፡፡ “ኧረ እባክህ ይሄ የአረፍተ ነገር አሰካክ መማሪያ እንጂ…” ብላችሁ ሳትጨርሱ “የፈለገ ዓረፍተ ነገር አሰካክ መማሪያ ቢሆንስ! ለምንድንው በሶ የሚሰጡት! ለምን አበበ ብርንዶ በላ አይባልም?” ብሎ አፍ አፋችሁን ሊላችሁ ይችላል፡፡ ደግሞላችሁ… “ጨቡዴ ጩቤ ጨበጠ…” በቃ ጨቡዴ ጩቤ ጨበጠ ማለት ነው — የአረፍተ ነገር አሰካክ መማሪያ፡፡

ዘንድሮ ግን የጨቡዴ ጩቤ መጨበጥ እንዲህ በቀላሉ የሚታለፍ ነገር አይደለም። ልክ ነዋ…“ካልጠፋ ነገር አበበ በሶ እየበላ፣ ጨቡዴን ጩቤ ማስጨበጥ ጨቡዴ ማፊያ ነው ለማለት ነው!” ምናምን የሚሉት አይነት ‘የደወሉላቸውን’ ሰው የማጣት ነገር አለላችሁ፡፡ ስብሰባ ተቀምጠን (‘ተኝተን’ ላለማለት ነው) የሚያበቃበት ሰዓት እንደ ‘ሚሊኒየሙ ግብ’ ርቆብን እያለ…አለ አይደል… ሰብሳቢው ምን ይላል መሰላችሁ…“በእውነቱ የተካፋዮች ንቃት የሚያስደስት ነው…” ኧረ በህግ አምላክ! (በነገራችን ላይ “በህግ አምላክ” ማለት ትልቅ የመብት ማስከበሪያ የነበረበት ዘመን እዚቹ እኛ አገር ውስጥ ነበር፡፡ የእውነት!) እናላችሁ… እኛ ጠቅላላ ‘ቫሊየም ፋይቭ’ እንደዋጠ ሰው እያንጎላጀጀን እያየ፣ ስለ ‘ንቃታችን’ ሲያወራ…አለ አይደል… አጠገብ ለአጠገብ ሆነን ‘የደወልንላቸውን ሰዎች’ ማግኘት እያቃተን ነው፡፡ ስብሰባ ላይ ከማንጎላጀጅ የባሰ ምን አይነት መደወል ይኖራል፡፡

ይቺን ስሙኝማ…በኮሚኒስት ሩስያ የኬጂቢ ጆሮ ጠቢ የሆነ ሰው ወደ አለቆቹ ይሄድና “ጎረቤቶቼ ከምዕራባውያን ጋር ግንኙነት አላቸው ብዬ እጠረጥራለሁ” ሲል ሪፖርት ያቀርባል፡፡ አለቃውም “በምን አወቅህ?” ሲል ይጠይቀዋል። ምን ብሎ ቢመልስ ጥሩ ነው… “በየቀኑ እራታቸውን ይበላሉዋ!” እኔ የምለው…ካነሳነው አይቀር፣ የኮንዶሚኒየም ነዋሪ ወዳጆቼ እንደሚነግሩኝ ከሆነ…“በየቀኑ እራታቸውን ይበላሉዋ!” አይነት ‘ጆሮ በግድግዳ’ ነገር በሽ፣ በሽ ነው አሉ፡፡ እኔ የምለው… ከአኗኗር ጋር እኮ መለወጥ ያለባቸው አንዳንድ ባህሪያት አሉ አይደል እንዴ! የአፓርትማ ኑሮ እኮ… (ኮንዶሚኒየም ማለትም ያው አፓርትማ ማለት ነው…) የ‘ፕራይቬሲ’ ኑሮ ነው፡፡ (ስሙኝማ…ግድግዳ ላይ የተለጠፈ ጆሮ እንዳይሰማን ንግግራችንን በጽሁፍ መለዋወጥ እንችላለን፡፡ ይቺ ቁና፣ ቁና ትንፋሿስ! በቃላት አትጻፍ ነገር! ቂ…ቂ…ቂ… ጥያቄ አለን፣ ቀጥለው በሚሠሩ ኮንዶሚኒየሞች ‘ሳውንድ ፕሩፍ ቤድሩም’ ይሠራልን!) እናላችሁ…ምን ያደርጋል አንዳንድ ነገር…አለ አይደል… ሳያቀስ እንደማይለቀው ያዳቆነ ‘ሉሲፈር’ ነክሶ ይይዝና አይለቅም፡፡

እናላችሁ… ከሳፋና ከድስታችን ጋር የሰፈር አዋዋል ያልተጻፉ ‘ፕሪንሲፕሎቻችንም’ ተከትለውን ፎቅ ላይ ይወጣሉ፡፡ ልክ ነዋ…ቅድመ-ኮንዶሚኒየም እኮ… አለ አይደል… ላይ ሰፈር ያለነው ታች ሰፈር ስላለችው እንትናዬ “ምን አግኝታ ነው ዛሬ እንዲህ ያማረባት!” አይነት ነገር እንላለን፡፡ ታች ሰፈር ያሉት እነእንትና ደግሞ ላይ ሰፈር ያለነውን … “ትናንት ሥጋ ወጥ ሲሸተን ነበር፣ ዛሬ ደግሞ ቋንጣ ፍርፍር…ይሄ ሁሉ ሥጋ ከየት እየመጣ ነው!” ሊሉን ይችላሉ። እናላችሁ…ይሄ ይሄ ተከትሎን ፎቅ ላይ እየወጣ ችግር እየሆነብን ነው፡፡ ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…የኮንዶሚኒየም ነገር ካነሳን አይቀር አንድ ወዳጄ ያጫወተኝን ስሙኝማ… (ወዳጄ፣ ባለማስፈቀዴ ሂሴን ውጫለሁ…)…እሱና እሷ ኮንዶሚኒየም ሦስተኛ ፎቅ ላይ ይኖራሉ፡፡ እናላችሁ… አየሩ ፀሀያማ ከሆነ መስኮቱን ከፍተው ወደየሥራቸውና ወደየጉዳያቸው ይሄዳሉ፡፡ ታዲያላችሁ… ቴሌቪዥኑ የተቀመጠው መስኮቱ አጠገብ ነው፡፡ አንድ ቀን ታዲያ እነሱ በሌሉበት ዝናብ ይመጣና ወጨፎው ቴሌቪዥኑን ያረጥበዋል፡፡

ሰውየው ተናዶ… “ለምንድነው መስኮቱን ሳትዘጊው የሄድሽው!” ምናምን ብሎ ይጮህባታል፡፡ እሷም ምን ብትል ጥሩ ነው… “እኔ ምን ላድርግ፣ ሬዲዮ ነው ያሳሳተኝ!” ትላለች፡፡ ለምን መሰላችሁ… ለካስ ጠዋት የአየር ጠባይ ትንበያው ላይ “ዛሬ አዲስ አበባ ከፊል ደመናማ ሆና ትውላለች…” ተብሎ ነበር። አሪፍ አይደል! ልክ ነዋ… ቢያንስ በአየር ጠባይ ትንበያ መሠረት የሚንቀሳቀስ ሰው መኖሩን ማወቅም አሪፍ ነው፡፡ እናላችሁ…ዘንድሮ “…የደወሉላቸውን ደንበኛ አሁን ማግኘት አይችሉም…” ነገር በየቦታው ያልተጻፈ መመሪያ አይነት ነገር ሆኖላችኋል፡፡ ስሙኝማ…ጋብሮቮዎች ሁለት ጊዜ ያልባቸዋል ይባላል፡፡ አንድ ጊዜ ፀሀይ ሲበዛባቸውና ሌላ ጊዜ ደግሞ ገበያ ሄደው ዋጋ ሲከራከሩ፡፡ እኛ አለን እንጂ… ‘እንትን በሚያሳቅፈው’ ብርድ ሁለት መቶ ሁለት ጊዜ የሚያልበን! ለምን አትሉኝም… በየሄድንበት ‘የደወልንላቸውን ማግኘት’ እያቃተን! ለክፉም ለደጉም በዚህ በበዓል ሰሞን የደወልንላቸውን እንዳናገኝ የሚደነቀሩ ደንቃራዎችን አንድዬ ከመንገዳችን ላይ ዘወር ያድርግልንማ! ስሙኝማ…በዛ ሰሞን በበሬ ሥጋ ውስጥ የፈረስ ሥጋ እየቀላቀሉ ሸጡ ምናምን ተብሎ አውሮፓ ታምሶ ነበር፡፡ ለነገሩ ግርግሩ ለምን ቀላቀሉብን ነው እንጂ ፈረሱንም፣ በሬውንም ስልቅጥ አድርገው ነው የሚበሉት፡፡

(እኔ የምለው…እነሱ እኮ የምግብ እጥረት የማይገጥማቸው…አለ አይደል… በመሬት የሚሄደውም፣ በሰማይ የሚበረውም፣ በባህር የሚዋኘውም አንዱም ሳይቀራቸው “እነሆ በረከት” ስለሚሉ ነው! አሀ.. እኛ ‘ቋቅ’ ሲለንስ! አይደለም… የምድር ላይ ተሳቢ ምናምን ‘አውሬ’ ሥጋ፣ አሁንም እኮ ፓስታ ‘ቋቅ’ የሚላቸው የገጠር ሰዎች መአት ናቸው!) እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ፣ ይቺን ስሙኝማ…የፈረንጁ ልኳንዳ ነጋዴ የፈረስ ሥጋ ከሌላ ሥጋ ጋር ቀላቅሎ ሲሸጥ ተገኘና ፍርድ ቤት ቀረበ፡፡ ዳኛው “ህዝቡ ሳያውቅ የፈረስ ሥጋ በመሸጥ ተከሰሃል፣ ምን መልስ አለህ?” ይሉታል፡፡ እሱ ሆዬም ምን ይላል…“ክቡር ዳኛ፣ ለነገሩ የፈረስ ሥጋ ብቻ አይደለም የሸጥኩት፡፡ ግማሽ የፈረስ ሥጋና ግማሽ የጥንቸል ሥጋ እየቀላቀልኩ ነው የሸጥኩት፡፡” ዳኛውም… “ጥሩ፣ ለመሆኑ ለአንድ ፈረስ ስንት ጥንቸል ቀላቀልክ?” ሲሉት እሱ ምን ቢል ጥሩ ነው… “ክቡር ዳኛ፤ ግማሸ ለግማሽ አልኩ እኮ፣ ማለት አንድ ፈረስ ለአንድ ጥንቸል፡፡” አሪፍ አይደል! ስሙኝማ… ለነገሩ ጊዜያችን የማይታሰቡ ነገሮች ሁሉ የሚሠሩበት ስለሆነ የምትሸምቱትን ሥጋ በደንብ እያያችሁ ግዙማ! ሁሉም ነገር በልክ ቢሆን አሪፍ ነው፡፡ የሁሉንም ነገሮች ‘ትንሳኤ’ ያፋጥንልንማ! መልካም የበዓል ሰሞን ይሁንላችሁማ! ደህና ሰንብቱልኝማ!

የመኢአድ ሊቀመንበር ኢ/ር ኃይሉ ሻውል ስለገዢው ፓርቲ ምን ይላሉ?

  • “ከ97 ወዲህ ፍርሃት የተጠናወተው ፓርቲ ሆኗል”
  • “ተቃዋሚ ፓርቲዎች ውስጥ ሰላዮችን አሰማርቷል”
  • “ምርጫኮ የለም ፤ ያለተወዳዳሪ ምረጡኝ ይላል”

በአገራችን የምርጫ ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ ቦታ በሚሰጠው የ97 ምርጫ ቅንጅትን በከፍተኛ ደረጃ ይመሩ የነበሩት እና በአሁኑ ሰዓት የመኢአድ ሊቀመንበር የሆኑት ኢ/ር ኃይሉ ሻውል፤ መጽሐፍ ይጽፋሉ ተብሎ ከተጠበቀበት ጊዜ ዘግይተውም ቢሆን “ህይወቴና የፖለቲካ እርምጃዬ” የሚል መጽሐፍ ለንባብ ሊያበቁ ተቃርበዋል፡፡ መጽሐፉ 200 ገጽ ያለው ሲሆን ቀጣይነት አለውም ተብሏል። ኢ/ሩ በእንግሊዝኛም ሰፋ ያለ መጽሐፍ እየፃፉ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡ በአዲሱ መጽሐፋቸው፣ በአገሪቱ ፖለቲካዊ ሁኔታና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ከኢንጂነር ሃይሉ ጋር ተከታዩን ቆይታ አድርጋለች፡፡

ኢንጂነር ኃይሉ፣ ስለገዢው ፓርቲ ምን ይላሉ? እስቲ በህትመት ላይ ስላለው መፅሀፍዎ ይንገሩኝ…. እንግዲህ የአንድ ሠው ታሪክ ብዙ ቅርንጫፎች አሉት፡፡ የእኔ ዋናው ቅርንጫፍ በሙያዬ የተሠማራሁበት ሥራ ነው፡፡ ነገር ግን የፖለቲካ ችግር ሲመጣ ወደ ፖለቲካ ገባሁኝ፡፡ እናም በፖለቲካ ጉዳዮች ዙሪያ ሰው እውነቱን እንዲያውቅ ቀለል ባለ መልኩ ፅፌዋለሁ፡፡ ብዙዎች በተለይ ፖለቲካውን በተመለከተ መጽሐፍ ለማውጣት እንደዘገዩ ይናገራሉ፡፡ የዘገዩበት ምክንያት ምንድን ነው? መፅሀፉ የዘገየበት ምክንያት የሚቀሩትን ላካትትበት ወይስ አሁን ያለቀውን ላሳትመው በሚለው ላይ ሳመነታ ነው፡፡ አሁን እየታተመ ያለውን ግን ከጨረስኩት ቆይቻለሁ፡፡

ግን ያለቀው ይውጣና ቀጣይ ክፍል አዘጋጅለታለሁ ብዬ ወሰንኩ። መቼም መፅሀፉ የ97ቱን ምርጫና የቅንጅትን ጉዳይ ማካተቱን አይቀርም፡፡ እስከዛሬ በቅንጅት ዙሪያ ከተፃፉት መፅሀፍት ምን የተለየ ነገር ይኖረዋል? እኔ እምናገረው እውነት ብቻ ነው፡፡ ከዚያ ውጭ የለም፡፡ እስከዛሬ ያየኋቸው መፅሀፍት ላይ ወገናዊነት አያለሁ፡፡ አንዳንዶቹ ላይ ደግሞ ከሚገባው በላይ ዘለው የሄዱ ጉዳዮች አሉ። ለምሳሌ የቅንጅት መፍረስ በቅንጅት መሪዎች ሲመኻኝ ነው የምሠማው፡፡ ነገር ግን የዚያ አይነት የፖለቲካ እመርታ ያመጣ ፓርቲ፤ በዚያ እሣት ውስጥ አልፎ የሄደ እንደመሆኑ መጠን ጥፋት ቢኖረው እንኳን ታይቶ ይታለፋል፡፡ አንዳንዶች ግን “እርስ በእርሣቸው ፈራረሱ” ይላሉ፡፡ ወያኔም እንዲህ ነው የሚለን፡፡ በጣም ያሣዝነኛል፡፡

እርስዎ ቅንጅትን ማነው ያፈረሠው ይላሉ?

እውነት ለመናገር ቅንጅትን ወያኔ ራሱ ነው ያፈራረሠው፡፡ አሁንም እያፈረሠ ነው፡፡ እያንዳንዱ ፓርቲ ውስጥ ቢያንስ ቢያንስ አስርና አስራ አምስት ያህል ሠላዮች አሠማርቷል፡፡ እኛም ወስጥ ተሠማርተው ስራቸውን ሲሠሩ ቆይተዋል፡፡ የእኛ ጥፋት ምኑ ላይ መሠለሽ፣ ዴሞክራሲ ብለን ስለተነሣን በየአካባቢው ያለው ሁኔታ ዴሞክራቲክ ነው በሚል ራስን በሚደልል ሁኔታ ግልፅ ሆንን እና ምስጢር የሚባል ነገር መያዝ አልቻልንም፡፡ በፊት ለፊት ስንሠራ ስለነበር ለወያኔ ተመቸነው፡፡

ተመቸነው ሲሉ እንዴት ነው?

የተመቸነውማ ውስጣችን ሆኖ እርስ በእርስ እንድናከስ አደረገ፡፡ የምንሠራውን ፕላን አስቀድሞ ማወቅ ቻለ፡፡ በውስጣችን እኛን የሚቃረን አዘጋጀ። አንድ ድርጅት ውስጡ ሆኖ የሚበትነው ወገን ሲኖር፣ ማን አፈረሰው ሊባል ነው! አፍራሾቹን ያሠማሯቸው አካል ነው ተጠያቂው፡፡ ራሣቸውን መስዋዕት አድርገው ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር የተሰለፉት አመራሮች ቅንጅትን አላፈረሱትም፡፡ ይህ በደንብ እንዲታወቅ እፈልጋለሁ፡፡

አሁን የነገሩኝ ሀሣብ በመፅሀፍዎ ውስጥ ተካትቷል?

አዎ! አካትቸዋለሁ፡፡ መፅሀፉ ስለቅንጅት መፍረስ፣ በአጠቃላይ ስለ ፖለቲካው ሁኔታ የሚዳስስ እንደመሆኑ፣

ምን ምን አዲስ ነገሮችን ይፋ ያደርጋል?

ከመነሻው ጠቅላላ ሂደቱን ይተነትናል፡፡ መጀመሪያውኑ ቅንጅትን ስንመሠርት አንዳንድ ችግሮች መኖራቸውን ሳላስተውል ቀርቼ አልነበረም። ነገር ግን “ግዴለም አብረን ስንሠራ ቀስ በቀስ ይስተካከላል” በሚል አምኜ አብሬ ተጉዣለሁ። ያንን ጉዳይ አሁን ላይ ሆኜ ወደ ኋላ ሳየው “ለምን ሳናጣራ ሄድን” ብዬ እጠይቅና እቆጫለሁ፡፡ ይሁን እንጂ ግዜው አይፈቅድም ነበር፡፡ ህዝብ ከእኛ ብዙ ይጠብቅ ነበር፡፡ የጋዜጦችም ግፊት ከፍተኛ ነበር፡፡ የዛን ጊዜ ወደ ኋላ ብንል ኖሮ “መኢአድ እንደልማዱ ቅንጅት አንፈጥርም ብሎ ነገር አበላሸ” ይባላል በሚል ነው የቀጠልነው፡፡ ምክንያቱም መኢአድ ባይኖር ቅንጅት አይፈጠርም ነበር፡፡ ይሄ ግልፅ ነው።

እንዴት?

ትልቅ ፓርቲ ተብሎ የተመሠረተው፣ ገጠሩንም ከተማውንም ያገናኝ የነበረው መኢአድ ብቻ ነበር። ሌሎቹ አብረውን የተጓዙት ፓርቲዎች አዳዲስ ነበሩ። አዲስ ተመስርተው ደግሞ ህዝብን ይዘን መጣን ማለት አይችሉም፤ አዲስ ከሆኑ ህዝብ የሚባል ነገር የላቸውማ! ይሁን እንጂ የእነርሱም ስራ ከፍተኛ እንደነበር አንክድም፡፡ ምክንያቱም ብዙው ምሁራን ስለነበሩ ህዝቡ በፓርቲው እምነት እንዲያገኝ በክርክሩ ጊዜ ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል። በአጭር ጊዜም ውስጥ ቢሆን ገብተው ብዙ የለውጥ መንገዶችን ያስተካከሉ ይመስለኛል፡፡ ነገር ግን በውስጣቸው ምን አይነት ሠዎች እንደተሠለፉ አልመረመርንም፤ ለዚህ ነው መፍረሱ የመጣው፡፡ ከኢህአዴግ ሌላ በውስጣችሁ ለቅንጅት መፍረስ ተጠያቂ የሆነ ወገን ነበር እያሉኝ ነው? ኢዴፓዎች ችግር ነበረባቸው፡፡

ከገዢው ፓርቲ ጋር በጣም የተጠጋጋ አሠራር ነበራቸው፡፡ መጨረሻ ላይም የታየው ይሄው ነው፡፡ እውነተኛው ጊዜ ሲደርስ የማፍረስ ሁኔታ የፈጠረው ኢዴፓ ነው፡፡

እና ኢዴፓ አፍራሽ ነው ብለው ያምናሉ ማለት ነው?

አምናለሁ! ይህንን ጉዳይ ማንም የሚክደው አይደለም፡፡ ግን እኮ መኢአድ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በክፍፍልና በንትርክ ውስጥ ነበር፡፡ የንትርኮቹ መንስኤዎች እና የመፍትሄ ሀሣቦች በመፅሀፉ ተካተዋል? አ…ይ…እሱ … ዛሬ ያለው ሂደት ከድሮው የተለየ አይደለም፡፡ ጠበቅ አድርገን ቤቱን ባናፀዳው ኖሮ፣ ዛሬ መኢአድ የሚባል ድርጅት አይኖርም ነበር፡፡ ልክ እንደ ሌሎቹ ከገዢው ፓርቲ ጋር ተጨባብጦ የሚኖር ድርጅት ለመመስረት ነበር የተፈለገው። ይህ ማለት ደግሞ ከህዝብ ጋር የሚቆም ፓርቲ አይኖርም ነበር ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ያንን ለመቀየር ብዙ የውስጥ ትግል አድርገናል፡፡ ይህንን ጉዳይ በሁለት ዙር ትግል ያፀዳነው ይመስለኛል፡፡ ከዚያ በኋላ አንድ ሁለቱ ቢራኮቱ ለእኛ ምናችንም አይደለም። እኛ የሚደበቅ ነገር የለንም እንጂ ሰላዮቹ ዛሬም አሉ፣ እናውቃቸዋለን፡፡

ዴሞክራቲክ ድርጅት እንደመሆናችን መሣሪያ በዚህ መጣ፣ ሠው በዚህ ተዋጋ የምንለው ነገር ስለሌለ የምንፈራው ነገር የለም፡፡ ሁሌ የሚሠልሉን ድንገት እነዚህ ሠዎች ወደ ሌላ ነገር ይገባሉ ብለው በመፍራት ይመስለኛል። በ97 ምርጫ በሠባ ምናምን እድሜዬ “ሠላማዊ ትግል ይዘን አሸነፍን፡፡ አቅማችንንም አወቅን። ከዚያ በኋላ ያለውን እኮ ለወጣቱ ትውልድ “ያውልህ” ብሎ ማስረከብ ነው፡፡ ወጣቱ ደግሞ የራሱን ስትራቴጂ አውጥቶ ይሄዳል፡፡

አሁን ያለው አጠቃላይ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ምን ይመስላል?

የፖለቲካ እንቅስቃሴ አለ እንዴ? እኮ አለ እንዴ? እርስዎ ይንገሩኝ … እኔ እንግዲህ ያለውን ሁኔታ እንቅስቃሴ አልለውም፤ አይደለምም፡፡ ነገር ግን በእኛ በኢትዮጵያ አንፃር ከሆነ ትንሽ መንፈራገጥ ጀምሯል፡፡ ሚያዝያ ስድስትና አስራ ሶስት ስለተካሄደው የአካባቢና የአዲስ አበባ ምርጫ ምን አስተያየት አለዎት? “ምርጫ” የሚለውን ቃል ለምን ተጠቀምሽበት? አባከንሺው እኮ፡፡

ለመሆኑ ምርጫ የሚባል ነገር ተደርጓል እንዴ?

አልተደረገም ነው የሚሉኝ?

አልተደረገም!! ድምፅ ሲሰጥ የምለውስ ሰው? ኢህአዴግ ወረቀት አሠባሠበ እንጂ ምንም ያደረገው ነገር የለም፡፡ ምርጫ ማለት ውድድር ሲኖር ነው፤ ከተወዳዳሪዎች መሀል ትመርጫለሽ። ዝም ብሎ “ኑ እኔን ምርጡኝ፤ ሌሎቻችሁ ዞር በሉ፣ ራሴ እመርጣለሁ፤ እራሴ እንደ ፈለግሁ አደርጋለሁ፤ ራሴ እናገራለሁ፤ ሌሎቻችሁ አፋችሁን ዝጉ” እየተባለ የሚደረግ ምርጫ በዓለም ላይ አይቼ አላውቅም፡፡ ከ97 ወዲህ ፍርሀት የተጠናወተው ፓርቲ ነው ስልጣን ላይ ያለው፡፡ ስለዚህ አንድም ፓርቲ እንዲነቃነቅ አይፈልግም፡፡ እኛም ደግሞ ወጣቱን ማስጨረስ አንፈልግም፡፡ ግዴለም ወቅቱ ሲደርስ ህዝቡ መልሱን ይሠጣል ፡፡ ከ2002ቱ ምርጫ ቀደም ብሎ በገዢው ፓርቲና በተፎካካሪ ፓርቲዎች መካከል የምርጫ ሥነ-ምግባር ኮድ ፊርማ ተካሂዶ ነበር፡፡ ኮዱን ከፈረሙት ፓርቲዎች መካከል መኢአድ አንዱ ነበር፡፡ በፊርማ ስነ-ሥርዓቱ ላይ እርስዎ ሲፈርሙ በቦታው ነበርኩኝ፡፡ የፊርማውን አስፈላጊነት በተመለከተ ጥያቄ ቀርብዎሎት የሰጡት መልስ ነበር፡፡ እስኪ አስታውሺኝ ልስማው… “እኛ ወደ ፊርማው የገባነው እየራቅን ነገሮች ከሚደበቁብን፣ ቀርበን የኢህአዴግን ልብ እና ሀሣብ ለማወቅ ነው፤ ጠላትን ወዳጅ መስሎ በመቅረብ እንጂ በመራቅ የሚገኝ ትርፍ የለም” ሲሉ ሠምቻለሁ፡፡ ከተፈራረሙና ከቀረቡ በኋላ ደግሞ ከስምምነቱ መኢአድ መውጣቱን አስታወቁ፡፡

ኢህአዴግን ቀርበውት የተማሩትና ያገኙት ቁም ነገር ምንድን ነው?

የምርጫ ስነ-ምግባር ኮድ መፈራረሙን በተመለከተ በመፅሀፍዎ ምን የሚነግሩን ይኖራል? መፅሀፏ መግለፅ ትገልፃለች፡፡ ኢህአዴግን በመቅረብ ምንም ያገኘነው ነገር የለም፡፡ ኢህአዴግ እስከ ዛሬ የኖረው ነገሮችን መደበቅ ስለሚችል፣ መሸፈን ስለሚያውቅበት ነው፡፡ እኛን መሣሪያ ለማድረግ ሞክሮ ነበር፡፡ እኛ አንቀጥልም ብለን ነው የወጣነው፡፡ ምክንያቱም እነሱ የሚያቀርቡት አጀንዳ እኛ ከምናቀርበው ጋር ምንም ግንኙነት የለውም፡፡ እኛም እንድንናገር አይፈለግም፤ ራሱ ምርጫው የልጆች ጨዋታ ነበር ማለት ይቻላል። መጀመሪያውኑም አውቀነዋል፡፡ ነገር ግን “እነዚህ ሠዎች ሠው ለመሆን ፈልገዋል፤ እድል እንስጣቸው ብለን ነው የገባንበት፡፡” ለካ እነሱ ይህንን ሁሉ የቀመሙት ምንም ፋይዳ ለሌለው ነገር ነው። እነሱ በፊትም እንደጀመሩት ወጣቱን አሣደው ጨርሠዋል፤ በየቦታው አስረዋል፣ በዚያው ነው የቀጠሉት፡፡

ታዲያ እንድንፈራረም ለምን ፈለጉ ብዬ ራሴን ስጠይቅ ላገኝ የቻልኩት አንድ ምክንያት ብቻ ነው፡፡ ምንድነው ምክንያቱ? ምክንያቱ ምን መሠለሽ፤ የአውሮፓ ታዛቢዎች አንመጣም ሥላሉ ይህን አይነት ሥምምነት እንዲፈረም ተደረገ፡፡ ከተፈራረምን በኋላ መጡ። ነገር ግን የአውሮፓ ታዛቢዎች በመምጣታቸው ኢህአዴግን የበለጠ ትዝብት ላይ ጣለው እንጂ ያተረፈበት ነገር የለም፡፡

ምክንያቱም ገጠር ድረስ ሄደን ምርጫውን እንዴት እንደሚያጭበረብር አሣይተናል፡፡ አስቀድመው የተዘጋጁ የድምፅ መስጫ ወረቀቶች ሳጥን ውስጥ ያስገቡ ነበር፡፡ ስለዚህ ምንም ላይጠቅም ነው ግርግር ሲፈጥር የነበረው፡፡

እርስዎ የምርጫ ስነ-ምግባር ኮድ በመፈራረምዎ ተፀፅተዋል?

የለም! አልተፀፀትኩም፡፡ ምክንያቱም ያቺ አንድ እድል ቀርታ እድል ሳልሠጥ ብቀር ነበር የሚቆጨኝ። ባልፈርም ነበር የሚቆጨኝ፡፡ ለምን ቢባል ያቺን ዕድል ሠጥተናቸዋል፤ አልተጠቀሙበትም፤ በጠላትነት ጉዟቸውን ቀጥለዋል፡፡ ስለዚህ ይሄ መንግስት በእርግጥ ዴሞክራሲ በፈቃደኝነት እንደማያመጣ አይተናል፡፡ እነዚህን ሂደቶች እንዳልኩሽ በመፅሀፉ ለማካተት ሞክሬያለሁ፡፡

በመጽሐፉ የተካተቱ ሌሎች ጉዳዮች ይኖራሉ?

መፅሀፉ አጭር ነው፡፡ ሌሎች ጉዳዮች በቀጣዩ መፅሃፍ ይካተታሉ፡፡ እነዚህን ሌሎች ጉዳዮች ከሠው ልጅ ኑሮ ጋር አገናኝቼ እየፃፍኩ ነው ያለሁት። ምክንያቱም ኢትዮጵያ ውስጥ የተደረገው ህዝቡን አደንቁሮ መግዛት ነው፡፡ ህዝብ ብዙ ጩኸት፣ ብዙ ወረቀትና ብዙ ግርግር ሲበዛበት፣ ዞር ዞር ብሎ አማራጭ ሲያጣ፣ ለጊዜው ኢህአዴግ ባመቻቸው መንገድ ብቻ ይሄዳል፡፡

በዛች መንገድ ሄዶ ግን መጨረሻው የማይበጀው መሆኑን ማወቁ አይቀርም፤ ያን ጊዜ ምን አይነት መልስ እንደሚሠጥ መገመት አያቅትም፡፡ ያ ጊዜ ደግሞ እየደረሠ ነው፡፡

የዚህች አገር የፖለቲካ እጣ ፋንታ ወዴት የሚያመራ ይመስልዎታል?

እኔ በአጠቃላይ ጥሩ ነገር አይታየኝም። የኢትዮጵያ ህዝብ ሠልችቶታል፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ይሄ ህዝብ ወያኔ እድል ይሠጠኛል ብሎ እንደማይጠብቅ እርግጠኛ ነኝ፡፡ የቀረው ሆ ብሎ መብቴን አስከብራለሁ ብሎ ሲነሣ፣ ያን ጊዜ ማን መልስ እንደሚሠጥ አናውቅም፡፡ በቃ ይሄው ነው፡፡ ይህን ሁሉ ፖለቲካ ፓርቲ የሚያራባው ማን ይመስልሻል፡፡ ዘጠና እና ዘጠና አምስት ፓርቲ አለ እኮ ነው የሚባለው፡፡

ለምሣሌ ሁለት ተቃዋሚ ፓርቲ ሲመሰረት ሌላ አራት ይፈጠራል። ማን ነው የሚፈጥራቸው ካልሽ ራሱ ወያኔ ነው የሚፈጥራቸው፤ ደሞዝ እየከፈለ የሚያኖራቸው ፓርቲዎች አሉ አይደለም እንዴ፡፡

እነማን?

በስም ይጠቅሱልኛል? አልጠቅስም! ራሣቸውን ጠይቂያቸው፡፡ የመንግስት ደመወዝ ተከፋዮች ስም ዝርዝር አለ። እሱን አንቺ ፈትሺ፤ “ኢንቨስትጌቲቭ ሪፖርቲንግ” የሚባል ዘርፍ አለ፡፡ እሱን ተጠቀሚ፤ እንደውም ጐበዝ ትመስያለሽ፤ እንደምንም ተሹለክልከሽ ታገኝዋለሽ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

በክልሎች ስለሚፈናቀሉ ዜጐች ብዙ እየተባለ ነው፡፡ ምን አስተያየትአለዎት?

በጣም አስቸጋሪ ጉዳይ ነው፡፡

አሁን ቤንች ማጂ ዞን ብትሄጂ አሠቃቂ ነገሮች አሉ፡፡ እኔ አሁን ጉዳዩን እንዲያጣሩ የላኳቸው፣ የአማራ ተወላጆች አይደሉም፡፡ ለምን ብትይ “አማራ ኬላ” የሚባሉ አምስት ቦታዎች አሉ፣ የአማራ ተወላጆች በነዚህ ኬላዎች አያልፉም፡፡ ስለዚህ ጉዳዩን እንዲያጣሩልኝ የደቡብ ሠዎች ነው የላኩት፡፡ መረጃ የደረሠኝም በደቡብ ተወላጆች በኩል ብቻ ነው፡፡ አማራ ቢሄድ በመታወቂያው ይያዛል፡፡

አምስቱም ኬላዎች ላይ ፖሊስ ቆሞ ይጠብቃል፡፡ምን ምን የሚባሉ ኬላዎች?

አሁን ዝርዝሩን አምጡልኝ አላልኩም ግን እነዚህ ኬላዎች አሉ፡፡ በእያንዳንዱ ኬላም ጠባቂ ሚሊሻዎች ቆመዋል፡፡ አንዳንድ አማራ ወደዛ የቢዝነስ ሥራ ኖሮት ለማለፍ ቢፈልግ “ አንድ ሺ ብር ክፈል” እንደሚባልም ደርሠንበታል፤ ጉቦ ነው እንጂ መቸስ ደረሠኝ አይሠጠውም እኮ፡፡ ህዝቡ ተስፋ ቆርጧል፣ ሠልችቶታል፣ ከኢህአዴግ ጥሩ ነገር አይጠብቅም ብለውኛል፡፡

እርሶም ቢሆኑ ጥሩ ነገር አይታየኝም እያሉ ነው፡፡የሰላማዊ ትግሉ ፋይዳ ታዲያ ምንድነው?

የእኛ ፋይዳማ ወቅቱ ሲደርስ ህዝብ እንዳይፋጅ መጠበቅ ነው፡፡ እንዴት ብትይ … በየወረዳው ኮሚቴዎች አሉን፡፡ ድሮ ቢሮ ውስጥ ነበር፤ አሁን ቢሮ አንጠቀምም፡፡ ምክንያቱም ቢሮ ያለበት ቦታ ወያኔ ሄዶ ያስራቸዋል፤ ያፈርሣቸዋል፡፡ ስለዚህ ያለ ቢሮ እንሰራለን፡፡ ሥራችንም ህዝቡ ከገደብ በላይ እንዳይወጣ “ተወው ይደርሣል” በሚል ከፍጅት ማዳን ነው፡፡ ይሄው ነው፡፡

  1. 1ኛ) ምንም ልለውጣቸው የማልችላቸውን ነገሮች እንድቀበል፣ አደብ እንድገዛ እንዲያደርገኝ
  2. 2ኛ) ልለውጣቸው የምችላቸውን ነገሮች እንድለውጣቸው ድፍረቱን እንዲሰጠኝ
  3. 3ኛ) በ1ኛውና በ2ኛው መካከል ያለውን ልዩነት አውቅ ዘንድ ዕውቀት እንዲሰጠኝ! የፋሲካ ስጦታ

ጀርመናዊው ባለቅኔ ሺለር ስለዳሞንና ፒንቲያስ (የሊቁ የፓይታጐረስ ተማሪዎች ናቸው) ወዳጅነት የሚከተለውን ይለናል፡፡ እንደተረት ብንወስደው ለዛሬ ቀን ይሆነናል፡፡ ዲዮኒሶስ ለተባለው መስፍን፤ ካራ የያዘ ዳሞን የሚባል ወንጀለኛ ይዘናል ብለው ባለሟሎቹ ወደ ችሎቱ አቀረቡለት፡፡ መስፍኑም በግዛቴ ላይ አምፀሃል በሚል ሞት እንደሚገባው ገለፀለት፡፡ “ሞትን አልፈራም” አለው ዳሞን፡፡ “ሆኖም መሥፍን ሆይ! የሦስት ቀን ጊዜ ብትሰጠኝ ምህረት እንደሰጠኸኝ እቆጥረዋለሁ” አለው፡፡ “የሦስት ቀን ጊዜ ለምን ፈለግህ?” አለ መስፍኑ፡፡ “እህቴን ድሬ ለመመለስ ነው፡፡ እኔ ከቀረሁኝ የሚዋሰኝ ጓደኛ በመያዣነት አንተ ዘንድ በዋስነት እንዲቀመጥ አደርጋለሁ” ሲል ተናገረ፡፡ መሥፍኑም፤ “ሦስት ቀን ሸልሜሃለሁ፡፡ ከዚያ ያለፍክ እንደሆነ ግን፣ ጓደኛህ በመስቀል ላይ ይሰቀላል” አለው፡፡ ጓደኛውን ጠርቶ ይህንኑ ነገረው፡፡ ጓደኛውም ዋስ ለመሆን ፈቃደኛ መሆኑን ገለፀ፡፡ ዳሞን እህቱ ያለችበት ቦታ ሄዶ፤ ድል ያለ ሠርግ ደገሰ፡፡

ሠርጉን አሳክቶ ጉዞ ወደ አገሩና ዋስ ወደሆነው ወዳጁ መልስ አደረገ፡፡ እየተጥደፈደፈም መንገድ ቀጠለ፡፡ መንገድ ላይ ዶፍ ዝናብ ጣለና ወንዝ ሞላ፡፡ ወንዙ እስኪጐድል ይጠብቅ ጀመረ፡፡ በጅረቱ ዳር ተንከራተተ፡፡ ወንዙ ግን አልጐደለም፡፡ ታንኳም አልመጣ አለ፡፡ “ጀንበር ከጠለቀች ወዳጄ መሞቱ ነው” ሲል አሰበ፡፡ በወንዙ ዳር ተንበርክኮ ፀለየ፡፡ የውሃው መጠን መብዛቱ በቀጠለ ጊዜ፤ ካበደው ጅረት ውስጥ ዘሎ ገባ፡፡ ውሃው፤ በአምላክ ፈቃድ፣ ወደ ዳርቻው ጣለው፡፡ አምላኩን አመስግኖ ሩጫውን በከተማው አቅጣጫ ቀጠለ፡፡ ጥቂት እንደሄደ ግን ቀማኛና ሽፍቶች ብቅ አሉበት፡፡ ካራቸውን መዘው አስፈራሩት፡፡ “ንብረት የለኝም፡፡ ያለኝ ንብረት ነብሴ ብቻ ናት፡፡ ነብሴን ደግሞ ለንጉሡ መስጠት አለብኝ!” ቢልም ንቅንቅ አልል አሉት፡፡ ስለዚህ በፍጥነት ያንደኛውን ካራ ነጥቆ አንድ ሶስቱን ሲጥላቸው፤ የቀሩት እግሬ አውጪኝ አሉ፡፡ ውሃ ጥሙንና በረሃውን ተቋቁሞ እየበረረ እንደምንም አገሩ ደረሰ፡፡

ዘበኛውን አገኘው፡፡ እሱም “በከንቱ አትልፋ፡፡ ወዳጅህን ለማዳን አትችልም፡፡ ይልቅ የራስህን ነብስ አድን” አለው፡፡ “ግዴለም የጣርኩትን ያህል ጥሬ ልደርስለት እሞክራለሁ፡፡ ካልሆነም በምድር ፍቅርና ዕምነትን አስተምሬ፤ በሰማይ ቤት አገኘዋለሁ” ብሎ ወደከተማው ማህል ዘለቀ፡፡ ህዝቡ የስቅላቱን የመስቀል እንጨት፣ ከቦ ቆማል፡፡ ወዳጁን በገመድ ሲስቡት አየ፡፡ “እኔን ስቀሉኝ! ለወዳጄ ደርሼለታለሁ!” አለ፡፡ ህዝቡ ጉድ አለ ጓደኛሞቹ ከስቅላቱ እንጨት ሥር ተቃቀፉና መላቀስ ጀመሩ፡፡ ሰው ሁሉ አብሮዋቸው አለቀሰ፡፡ መሥፍኑ ይሄን ተዓምር ሰምቶ ሰብዓዊ ርህራሄ ተሰማው፡፡ ወደዙፋኑ አስጠራቸውና፤ “የፈለጋችሁት ይሄው ሆነላችሁ ሌላ ነገር ሳይሆን ልቤን ማረካችሁ፡፡ ልመናዬን ስሙኝ እባካችሁን በማህበራችሁ ሶስተኛ ልሁን” ሲል ተቀላቀላቸው፡፡

                                                          * * *

ለጓደኛ ሲሉ መሥዋዕት መሆን ታላቅ ነገር ነው! ዕውነተኛ ፍቅር የሚመጣውና የሚረጋገጠውም ለሌሎች ለማለፍ ዝግጁ ከመሆን ነው፡፡ ያለንን ፍቅር በመስጠት የሌሎችን ልብ መርታት የድሎች ሁሉ ድል ነው! ፋሲካን በዚህ መንፈስ ማክበር ታላቅ ፀጋ ነው!! በዓሉ የሁላችንም እንዲሆን የታረዘ ይልበስ፡፡ የታሰረ ይፈታ፡፡ የነገደ ይቅናው፡፡ የተማረ ይወቅ፡፡ የቦለተከ የህዝብ ዳኝነት ያግኝ፡፡ የተሰሩ መንገዶች ቀና መራመጃ ይሁኑ፡፡ “ፈጣን ነው ባቡሩ” ያልነው ተሳፋሪዎችን ጥሎ አይብረር፡፡ “ያልተመለሰው ባቡር” አዲሱን ባቡር አይማ! ፋሲካው፤ ስቅለትን፣ እሾህ - አክሊልን፣ ግርፋትን፣ ህመምን ያሳየንን ያህል፤ ትንሣዔን እርገትን፤ ለሌሎች ስንል መስዋዕት መክፈልን ያስተምረን ዘንድ፤ ሀገራችንን ህዝባችንን እንድናስብ ልቡናውን ይስጠን፡፡ የኑሮ ውድነትን ለዓመታት ያየነው መሆኑን አንዘነጋም፡፡ የዛሬ ገበያ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ፤ የተጠራቀመ መሆኑንም ልብ ማለት ያባት ነው፡፡ ሆኖም የባሰ አታምጣን እንፀልይ! በዓሉን በደስታና በፌሽታ ለማክበር ያለን ጓዳ - ጐድጓዳ ቆፍሮ፣ የመሶብን ተቃምሶ፣ “ከዓመት ዓመት አድርሰን” ማለት ለባዩም ለሚባለውም አንዳች የሁለትዮሽ ፀጋ እንደሚያጐናጽፍ አይታበልም፡፡

ይሄንን በባዶ አንጀት የማለት አቅም ላጣው ማዘን፣ መባባት ተገቢ ነው፡፡ በሀሰት መስክረው እንዲሰቀል ያደረጉትም ሆነ፤ ከደሙ ንፁህ ነኝ” ያለውም፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ አሳልፎ የሰጠውን፣ የይሁዳን ድርጊት የፈፀመና፤ በሰው ልጆች ላይ ግፍና በደል ይፈፀም ዘንድ ድንጋይ ያቀበለ የእጁን ይስጠው፡፡ ድንጋይ የመረጠም ሁሉ፤ የእጁን አይጣ! ዓይነተኛ መማሪያ ሆኖ፤ ልንጠበብ፣ ልንጠነቀቅና መንፈሳዊ ትንሣዔን ልናገኝ ይገባል፡፡ በዓሉ የፌሽታና የደስታ የሚሆንልን ልባችን ንፁህ ሲሆን ነው፡፡ ልባችን ንፁህ የሚሆነው እጃችን ንፁህ ሲሆን፣ አዕምሮአችን ከግፍ የፀዳ ሲሆን፣ ቃል የገባነውን ለመፈፀም ነፃ አስተሳሰብ ሲኖረን፣ ኃጢያትን ፈርተን ሳይሆን ዲሞክራሲ እንዲዋሃደን ስንወድ፣ ፍትህ ለሰው ልጅ እኩልነት መገለጫ፣ የሌሎች ደስታ ደስታዬ ነው መባያ እንዲሆን ማድረግ ማለት ነው፡፡ ስንበላ የማይበሉትን እናስባቸው፡፡ ስንናገር የማይናገሩትን እናስባቸው፡፡ ስናሸንፍ የተሸነፉትን እናስባቸው፡፡ ስንገዛ የተገዢዎቹን መብትና ነግ በእኔን እናስብ፡፡ ስለትንሣዔ ስናስብ ስለኢትዮጵያ ትንሣኤም በስፋት እናስብ!! መልካም ትንሣዔ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ!!

ለ58ኛዋ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫ ጀርመንን የወከሉ ሁለት ክለቦች ለፍፃሜ ጨዋታ መድረሳቸው የቦንደስ ሊጋን የበላይነት አረጋገጠ፡፡ ከ3 ሳምንት በኋላ የቦንደስሊጋ ደርቢ የተባለውን የሻምፒዮንስ ሊግ የፍፃሜ ጨዋታ የእንግሊዙ ዌምብሌይ ስታድዬም ሲያስተናግድ ቦርስያ ዶርትመንድ ከባየር ሙኒክ ይፋለማሉ፡፡ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የፍፃሜ ጨዋታ በ70 አገራት በ40 የተለያዩ የኮሜንታተር ቋንቋዎች በሚኖረው የቀጥታ ስርጭት ከ120 ሚሊዮን በላይ ተመልካች እንደሚያገኝ ታውቋል፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ ግማሽ ፍፃሜ ሁለቱን የስፔን ፕሪሚዬራ ሊጋ ክለቦች የጀርመን ቦንደስ ሊጋው ክለቦች 11ለ3 በደርሶ መልስ ውጤት አሸንፈዋል፡፡ በዘንድሮ የጀርመን ቦንደስሊጋ ሻምፒዮናነት ፍፁም የበላይነት የነበረው ባየር ሙኒክ በሜዳው አሊያንዝ አሬና ባርሴሎናን 4ለ0 ካሸነፈ በኋላ በመልሱ ኑካምፕ ላይ ባርሴሎናን በድጋሚ 3ለ0 በሜዳው አንበርክኮ በድምር ውጤት 7ሎ በመርታት ወደ ዋንጫው ማለፉን አረጋግጧል፡፡

የአምናው የቦንደስ ሊጋ ሻምፒዮን ቦርስያ ዶርትመንድ በበኩሉ የአምናው የፕሪሚዬራ ሊጋ ሻምፒዮን ሪያል ማድሪድን በሜዳው 4ለ1 ካሸነፈ በኋላ በሳንቲያጎ በርናባኦ 2ለ0 ቢረታም በአጠቃላይ ውጤት 4ለ3 በማሸነፉ ወደ ዋንጫው ፍልሚያ ተሸጋግሯል፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ የግማሽ ፍፃሜ የዓለም ስፖርት አፍቃሪ አራት አይነት የፍፃሜ ጨዋታዎችን ሲጠባበቅ ነበር፡፡ ከአራቱ ዓይነት የፍፃሜ ፍልሚያዎች ሊከሰት የበቃው ግን ባየር ሙኒክ ከቦርስያ ዶርትመንድ የሚፋጠጡበት የቦንደስ ሊጋ ደርቢ ነው፡፡ ሁለቱ የስፔን ክለቦች ባርሴሎና እና ሪያል ማድሪድ በሜዳቸው ባደረጉት የመልስ ጨዋታዎቻቸው ተጋጣሚዎቻቸውን ቢያሸንፉ ኖሮ ዋንጫው የኤልክላሲኮ ድግስ ነበረ፡፡ ሌሎቹ ሁለት ሊያጋጥሙ የሚችሉ የዋንጫ ፍልሚያዎች ደግሞ ባርሴሎና ከቦርስያ ዶርትመንድ ወይንም ሪያል ማድሪድ ከባየር ሙኒክ የሚገናኙባቸው እና ቦንደስ ሊጋን ከፕሪሚዬራ ሊጋ የሚያፋጥጡ ድራማዎችም ነበሩ፡፡

በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የቦንደስ ሊጋ ደርቢ ሲያጋጥም የመጀመርያው ነው፡፡ ከዘንድሮ በፊት በውድድሩ ታሪክ የአንድ አገር ተወካይ ክለቦች ለፍፃሜ የተገናኙት በ3 የዋንጫ ጨዋታዎች ላይ ነበር ፡፡ የመጀመርያው በ2003 እኤአ ላይ የሻምፒዮንስ ሊግ ፍፃሜ በፕሪሚዬራ ሊጋ ደርቢ ሪያል ማድሪድ ቫሌንሽያን 3ለ0 በመርታት ዋንጫ የወሰደበት ነበር፡፡ ሁለተኛው በ2005 እኤአ የሻምፒዮንስ ሊግ ፍፃሜ በጣሊያን ሴሪኤ ደርቢ ኤሲ ሚላን በመለያ ምቶች ጁቬንትስን 3ለ2 አሸንፎ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃበት ነበር፡፡ ሶስተኛው ደግሞ በ2008 አኤአ ላይ የሻምፒዮንስ ሊግ ፍፃሜ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ደርቢ ማን ዩናይትድ ከቼልሲ ጋር አገናኝቶ ፤በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ 1 እኩል አቻ ከተለያዩ በኋላ ማን ዩናይትድ በመለያ ምቶች 6ለ5 አሸንፎ ዋንጫውን ያነሳበት ነበር፡፡ በዘንድሮው የአውሮፓ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የግማሽ ፍፃሜ ምእራፍ ላይ ከጀርመንና ከስፔን የተወከሉ አራት ክለቦች ሲገኙ ከ13 አመታት በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ ነበር፡፡ ይህ ሁኔታ በአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች መካከል የነበረው የሃይል ሚዛን ከእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በመሸሽ ወደ ጀርመን ቦንደስ ሊጋ መጠጋቱን አረጋግጧል፡፡

የስፔን እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት አንጀላ ማርያ የግማሽ ፍፃሜው ትንቅንቅ ከፕሪሚዬራ ሊጋው እና ከቦንደስ ሊጋው የትኛው እንደሚልቅ ምላሽ ይሰጣል በማለት ተናግረው የነበረ ሲሆን ጀርመኖች ስታድዬሞች ቢኖራቸውም ምርጥ ውድድር ያለን ስፓንያርዶች ነን ብለው ፉክክሩን ለማሸነፍ ፍላጎት አሳይተው አልሆነላቸውም፡፡ የዘንድሮ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ግማሽ ፍፃሜ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ እና የስፔን ፕሪሚዬራ ሊጋ ንፅፅር ውስጥ በማስገባትም አከራካሪ ሆኖ ሰንብቷል፡፡ ከቦንደስ ሊጋ እና ከፕሪሚዬራ ሊጋው የቱ ይበልጣል በሚለው ክርክር ሚዛን ከደፉ አጀንዳዎች የሁለቱ አገር ክለቦች አጨዋወት የመጀመርያው ነው፡፡ የጀርመኑ ቦንደስ ሊጋ የመከላከል ስትራቴጂ በብሎኬት ግንብ የተመሰለና የማጥቃት ጨዋታው በከፍተኛ ወራራ የሚታጀብ መሆኑ ተገልጿል፡፡ የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋ ደግሞ በሚያምር የኳስ ቁጥጥር እና ቅብብል እንዲሁም በፈጠራ በተሞሉ የግብ አይነቶቹ ተፎካካሪነቱ ተጠቅሷል፡፡ ለጀርመን ቦንደስ ሊጋ ምርጥነት ግን ብዙ ምክንያቶች እየተዘረዘሩ ናቸው፡፡ በአካዳሚዎች ጥራት፤ በስታድዬም ዋጋ መርከስ እና በተመልካች መሞላት፤ በጤናማ የፋይናንስ እንቅስቃሴ የጀርመን እግር ኳስ የአውሮፓ ደረጃ በከፍተኛ ልዩነት እየመራ ይገኛል፡፡

ለዘንድሮ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ፍፃሜ በደረሱት ሁለቱ የጀርመን ክለቦች ከአካዳሚዎች የወጡ ከ10 በላይ ወጣት ተጨዋቾች ይገኛሉ፡፡ በባየር ሙኒክ ፊሊፕ ላሃም፤ ባስትያን ሽዋንስታይገር፤ ቶማስ ሙለርእና ዴቪድ አላባ እንዲሁም በዶርትመንድ ማርዮ ጎትሴዜ፤ ማርኮ ሬውስ እና ኑሪ ሳሂን በየክለቦቹ ከሚገኙ አካዳሚዎች የተመለመሉ ናቸው፡፡ የጀርመን እግር ኳስ ላይ በታዳጊ እና ወጣት ፕሮጀክት በስፋት መሰራት ከጀመረ ከ10 ዓመታት በላይ አልፏል፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ ደግሞ ከ713 ሚሊዮን ዩሮ በላይ እድሜያቸው 19 እና 20 የሚሆናቸው ምርጥ ፕሮፌሽናሎችን ለማፍራት ተችሏል፡፡ ስለሆነም ደግሞ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ ክለቦች በአገር ውስጥ ውድድር እና በአህጉራዊ ደረጃ በሚያሳዩት ስኬት ይሄው የአካዳሚዎች አስተዋፅኦ ጎልቶ ወጥቷል፡፡ ከወጣት ተጨዋቾች ባሻገር ከጀርመን ቦንደስ ሊጋ 18 ክለቦች ካንዱ በቀር በሁሉም እየሰሩ ያሉት አሰልጣኞች አገር በቀል መሆናቸው ሌላው ለእግር ኳሱ መጠናከር ምክንያት የሆነ ነው፡፡ በትርፋማነት የእንግሊዙ ፕሪሚዬር ሊግ ቀዳሚ ቢሆንም ቦንደስሊጋም በፍጥነት እያደገ ነው፡፡ 2013 ሲገባ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ 2.1 ቢሊዮን ዶላር ባንድ የውድድር ዘመን በሪከርድ ስኬት ገቢ አድርጓል፡፡ በሚቀጥለው የውድድር ዘመን ቦንደስ ሊጋው በቴሌቭዥን የስርጭት መብት የሚያገኘው ገቢ መጨመር ደግሞ የሊጉን ትርፋማነት ያሳድገዋል፡፡ የጀርመን ክለቦች የፋይናንስ ጤንነት እና የቦንደስ ሊጋው አስተዳደር 50 ሲደመር አንድ በሚለው ደንብ የክለቦች ባለቤትነት ድርሻን ለአባላት እንዲሆን ማስገደዱ ተመጣጣኝ አቅምና እና ፉክክር በውድድር እንዲኖር አድርጓል፡፡

የጀርመን ቦንደስ ሊጋ ጨዋታዎችን በስታድዬም ገብቶ ለመመልከት ያለው የትኬት ዋጋም ከሌሎች የአውሮፓ ሊጎች የረከሰ መሆኑም ሌላው ምክንያት ነው፡፡ አንድ የጀርመን ቦንደስ ሊጋን ጨዋታ ለመታደም ርካሹ የትኬት ዋጋ 12 ዩሮ ሲሆን ይህ ገንዘብ የትኛውንም የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ጨዋታ ለማየት አይበቃም፡፡ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የ58 አመታት የውድድር ታሪክ በሁለት ክለቦች 13 ዋንጫዎችን በመሰብሰብ የሚመራው የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋ ቢሆንም በ5 ክለቦች ተመሳሳይ የዋንጫ ብዛት በመሰብሰብ የእንግሊዙ ፕሪሚዬር ሊግ በሁለተኛ ደረጃ ይከተላል፡፡ የጣሊያኑ ሴሪኤ በ3 ክለቦች ባገኛቸው 12 ዋንጫዎች ሶስተኛ ደረጃ ሲይዝ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በ3 ክለቦች 6 ጊዜ የአውሮፓ ሻምፒዮን በመሆን በአራተኛ ደረጃ ላይ ነው፡፡ በክለብ ደረጃ 9 የሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫዎችን በመሰብሰብ የሚመራው የስፔኑ ሪያል ማድሪድ ሲሆን የጣሊያኑ ኤሲ ሚላን 7፤ የእንግሊዙ ሊቨርፑል 5 ዋንጫዎችን በመሰብሰብ ሁለተኛ እና ሶስተኛ ናቸው፡፡ ባየር ሙኒክ እና ባርሴሎና እያንዳንዳቸው አራት የሻምፒዮንስ ሊግ የዋንጫ ድሎችን በማስመዝገብ አራተኛ ደረጃ ሲወስዱ በተከታይነት የተመዘገበው ማን ዩናይትድ በሶስት የዋንጫ ድሎቹ ነው፡፡

ዶርትመንድ በ1 የሻምፒዮንስ ሊግ ድሉ በ22ኛ ደረጃ ላይ ተመዝግቧል፡፡ ታዋቂው የቢዝነስ መፅሄት ፎርብስ ይፋ ባደረገው የአውሮፓ ክለቦች የዋጋ ግምት ሪያል ማድሪድ በ2.532 ቢሊዮን ዩሮ ተመን አንደኛ ደረጃ ሲወስድ ማን ዩናይትድ በ2.429 ቢሊዮን ዩሮ ሁለተኛ ነው፡፡ በዚሁ የክለቦች የዋጋ ተመን ደረጃ ባርሴሎና በ1.995 ቢሊዮን ዩሮ ሶስተኛ ደረጃ ሲያገኝ ባየር ሙኒክ 1.017 ቢሊዮን ዩሮ በሚተመነው አርሰናል ተበልጦ በ1.005 ቢሊዮን ዩሮ የዋጋ ግምት አምስተኛ ደረጃን አግኝቷል፡፡ በአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር በሚሰጠው ነጥብ መሰረት ባለፈው የውድድር ዘመን የአውሮፓ ታላቅ ሊጎች በወጣላቸው ደረጃ 84.10 በማስመዝገብ የሚመራው የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ነበር፡፡ የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋ በ84.08፤ የጀርመኑ ቦንደስ ሊጋ በ75.18 እንዲሁም የጣሊያኑ ሴሪኤ በ59.81 ነጥብ እስከ አራት ያለውን ደረጃ አከታትለው ይዘዋል፡፡

በስታድዬም የአንድ ጨዋታ አማካይ ተመልካች የሚመራው የጀርመን ቦንደስሊጋ 45116 አስመዝግቦ ሲሆን የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ 34601 እንዲሁም የስፔን ላሊጋ 28403 ተመልካች በአንድ የሊግ ጨዋታ በማግኘት ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃ ይወስዳሉ፡፡ በአንድ የውድድር ዘመን በሚያስገኘው የገቢ መጠን የሚመራው የእንግሊዙ ፕሪሚዬር ሊግ ከ2.5 ቢሊዮን ዩሮ በላይ በመሰብሰብ ነው፡፡ በገቢ መጠን ሁለተኛ ደረጃ የሚወስደው 892 ሚሊዮን ዩሮ በአንድ የውድድር ዘመን የሚያስገባው የጣሊያኑ ሴሪኤ ውድድር ሲሆን የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋ በ560 ሚሊዮን ዩሮ እንዲሁም የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በ422 ሚሊዮን ዩሮ ገቢያቸው ተከታታይ ደረጃ ተሰጥቷቸዋል፡፡

መንግስት “ሽብርተኛ” ብሎ ከፈረጃቸው ድርጅቶች አንዱ የሆነውና በዶ/ር ብርሃኑ ነጋ የሚመራው የግንቦት 7 አባል በመሆን የፈንጂ ስልጠና ሰጥተዋል በተባሉት ሻለቃ ማሞ ለማና አቶ አበበ ወንድማገኝ ላይ የቀረበው ክስ ከትላንት በስቲያ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ተሰማ፡፡ በእለቱ በተነበበው የክስ መዝገብ ላይ አቶ አበበ ወንድማገኝ፤ በእንግሊዝ ሃገር ከሚገኙት ሻለቃ ማሞ ለማ ጋር በተደጋጋሚ በዱባይና ለንደን በመገኘት የፈንጂ ጥቃት ለማድረስ የሚያስችል ስልጠና በኤርትራ ወስደዋል ይላል፡፡

ወደ አዲስ አበባ ከተመለሱ በኋላ፣ ግለሰቦችን በመመልመል የትጥቅ ትግል ለማድረግ በማሰልጠን ለሽብር ተግባር አነሳስተዋል በማለት አቃቤ ህግ ባቀረበው ክስ፣ አቶ አበበ ወንድማገኝ ጥር 15 ቀን 2005 ዓ.ም ቦሌ ሰሚት አካባቢ መኪና ውስጥ 10 “c4” የተሰኙ ፈንጂዎችንና ማቀጣጠያ ገመዶችን ይዘው ተገኝተዋል ብሏል፡፡ የተከሳሽ ጠበቃ ባቀረቡት መቃወሚያ፤ የአቃቤ ህግ ክስ በየትኛው አዋጅ እንደቀረበ ክሱ እንደማያመለክት ጠቁመው፤ ደንበኛቸው የፈንጂ ስልጠና መስጠቱን እንዳልካደ በመግለፅ፤ አቃቤ ህግ ያቀረበው የክስ አንቀፅ እንዲያሻሽል ፍ/ቤቱን ጠይቀዋል፡፡

ስልጠና መስጠትን ብቻ የሚመለከት ስላልሆነ ራሱን አንዲያሻሽል ጠይቀዋል፡፡ አቃቤ ህግ በበኩሉ፤ የተከሳሽ ድርጊት በሰው ህይወት፣ በአካልና በንብረት ላይ ጉዳት ሊያስከትል የሚችል እንደነበር የሚያካትት ክስ እንዳቀረበ ገልጿል፡፡ “ተከሳሹ ስልጠና ብቻ ነው የሰጠው” የሚባለው ጉዳይ ማስረጃ የምናረጋግጠው ነው በማለት አቃቤ ህግ አክለው ገልፀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ብይን ለመስጠት ለፊታችን ሰኞ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

የአረብ ሃገር ተጓዧን ያታለሉት በእስራት ተቀጡ የ14 ዓመቷን የቤት ሠራተኛ የደፈረው 10 አመት ተፈርዶበታል በአዲስ አበባ ጐማ ቁጠባ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ሂሩት አጽበሃን “ሸርሙጣ” ብላ የሰደበችው ኪሮስ ሃይሉ በ15 ቀናት የጉልበት ስራ እንድትቀጣ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ተወሰነ፡፡ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት በቀረበው የክስ አቤቱታ ላይ እንደተመለከተው፤ ተከሳሽ የ50 አመቷ ወ/ሮ ኪሮስ ተበዳይን ሸርሙጣ፣ ሌባ፣ ቡዳ የሚሉ ስድቦችን የሰደበቻት ሲሆን ይህም በሰው ምስክር መረጋገጡ ተጠቁሟል፡፡ ፍርድ ቤቱም ድርጊቱ ደረጃ እና እርከን ያልወጣለት መሆኑን በመግለጽ፣ ተከሳሽ ለ15 ቀናት የግዴታ የጉልበት ስራ እንድትሰራ የወሰነ ሲሆን ውሳኔው በቀበሌ 12/14 እንዲያስፈጽምና ውጤቱን እንዲያሳውቅ ፍ/ቤቱ አሳስቧል፡፡ አቃቤ ህግ የቅጣት ማክበጃ ባለማቅረቡ እንጂ ቅጣቱ ከዚህም የከበደ ሊሆን እንደሚችል ተጠቁሟል፡፡

በሌላ በኩል ተከሳሾች ምስሬ ጌትነት መንግስቱ የተባለው ወጣት እና ግብረ አበሩ ሰዓዳ ሙሃቢን የተባለች ግለሰብ ላይ ለፈፀሙት የማጭበርበር ወንጀል እስራትና የገንዘብ ቅጣት ተበይኖባቸዋል፡፡ ሚያዚያ 2 ቀን 2005 ዓ.ም ከጠዋቱ 3 ሰዓት ላይ 1ኛ ተከሳሽ:- ሰአዳ ሙሃቢን የተባለች የግል ተበዳይን በተለምዶ አሜሪካን ግቢ በሚባለው ቦታ አግኝቷት ወደ ጋምካ እንደምትሄድ ስትገልጽለት፣ እኔም የእህቴን ዶክመንት ይዤ ልሄድ ነውና አብረን እንሂድ በማለት ጋምካ ከደረሱ በኋላ፣ ከ2ኛ ተከሳሽ ጋር በመሆን ተበዳይን ሁለት መቶ ብር ተከፍሎ የሚወሰድ ትኬት አለ፤ ይህን ትኬት ካልያዝን ማለፍ አንችልም፣ ትኬቱ ሲገዛም እቃ ወይም ንብረት ይዞ መግባት አይቻልም በማለት፣ ሁለተኛ ተከሳሽ ተበዳይዋን ይዟት ትኬት ይቆረጣል ወደተባለበት ቦታ ሲወስዳት፣ ሁለተኛ ተከሳሽ የግል ተበዳይ ይዛው የነበረውን 10,800 ብር፣ እንዲሁም 2ሺ 400 ብር የሚያወጣ ኖኪያ እና መታወቂያ ካርድ ተቀብሎ ከአካባቢው የተሰወረ በመሆኑ በአታላይነት ተከሰው በ1 አመት ከ3 ወር እስራት እና በ200 ብር እንዲቀጡ ተወስኗል፡፡

በዚያው በፌዴራል ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 7ኛ ወንጀል ችሎት በተሰጠ ሌላ ውሣኔ አቶ ተከስተ ዘሪሁን ለገሠ የተባሉት አባወራ በ26/01/2005 ዓ.ም ከሌሊቱ በግምት ስድስት ሰአት ሲሆን በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ልዩ ቦታ ኮንዶሚኒየም ተብሎ ከሚጠራው አካባቢ፣ የ14 አመቷን ህፃን የቤት ሠራተኛውን፤ ሚስቱ ያለመኖሯን በማረጋገጥ በሹራብ አፍኖ በመድፈር፣ ክብረንፅህናዋን በመገርሰሱ በፈፀመው ወንጀል በ10 ዓመት እስራት እንዲቀጣ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

(የአሜሪካውያን ነገር! መፍትሄ ይዞ ብቅ የሚል አይጠፋም። ሚቸል ክሮዝቢ፣ የፍቺ ወጪዎችን በሶስት እጅ የሚቀንስ ዘዴ በመፍጠር ቢዝነስ ጀምራለች።) አዲስ አበባ ውስጥ ሁለት መኖሪያ ቤት የነበራቸው ባልና ሚስት፣ በፍቺ ሲለያዩ የፈጠሩትን ፀብ ልንገራችሁ። እንደ ምርጫቸው አንድ አንድ መከፋፈል ይችሉ ነበር። ባል አንደኛውን ቤት መረጠ። ሚስት ምንም አልከፋትም። የመኖሪያ ቤቶቹ ዋጋ ተቀራራቢ ስለሆነ፣ ሌላኛውን ቤት መረጠች። በቃ? በጭራሽ! ሚስትዬው ያለምንም ጣጣ ስለተስማማች፣ ባልዬው በቁጭትና በእልህ ተነሳስቶ ሃሳቡን ቀየረ። እንለዋወጥ አለ - ሚስትን ለማሳረር በመመኘት።

የራሱን ጥቅም ሳይሆን፣ የሚስቱን ጉዳት ለማየት ነው የናፈቀው። በእርግጥ ሚስትዬው፣ አንደኛውን ቤት እስካገኘች ድረስ ግድ አልነበራትም። ግን እልህ ውስጥ ገባች፤ “አይሆንም!” አለች። ሁለቱን ለማስታረቅ ያልተደረገ ሙከራ ባይኖርም አልተሳካም። ስለዚህ መኖሪያ ቤቶቹ ተሸጠው በገንዘብ እንዲከፋፈሉ ተወሰነ። አቶ ባል፣ ነገርዬው እንዲህ እየከረረ እዚህ ደረጃ ላይ የሚደርስ አልመሰለውም ነበር። ግን፣ የተበላሸውን ነገር መልሶ ማስተካከል አይችልም። ቤት የሚገዛ ሰው ፈልገው ማምጣት አለባቸው፤ ወይም ደግሞ በፍርድ አፈፃፀም መስሪያ ቤት በኩል፣ በሃራጅ ቤቶቹ ይሸጣሉ። ያው፤ ለሃራጅ የቀረበ ንብረት ብዙም ዋጋ አያወጣም። ለዚህም ነው፤ ባልዬው ቤት የሚገዙ ሰዎችን አፈላልጎ ያመጣው። ይህን ሁሉ ጣጣ በመፍጠሩ የተበሳጨችው ሚስትዬው ግን ፈቃደኛ አልሆነችም። በሃራጅ ካልተሸጠ ሞቼ እገኛለሁ አለች። የራሷን ጥቅም ከማስላት ይልቅ፣ የባልዬውን መክሰር ለማየት ጓጉታለች።

ከፍርድ አፈፃፀም ሰራተኞች እንደሰማሁት፣ ቤቶቹ በሃራጅ ስለተሸጡ ሁለቱ ሰዎች ወደ 300 ሺ ብር ገደማ ከስረዋል። ከፍቺ ጋር አላስፈላጊ እልህ የሚፈጠረው በኢትዮጵያ ብቻ አይደለም። የትም አገር ቢሆን፣ ትዳር በፍቺ ሲፈርስ፣ ብዙውን ጊዜ አዲስ ጥላቻና ቂም ያበቅላል። ባለትዳሮቹን ለፍቺ ከገፋፋቸው ጥላቻ ይልቅ፣ ለመፋታት ከወሰኑ በኋላ በንብረት ክፍፍልና በልጅ አስተዳደግ ጉዳዮች ላይ ሲከራከሩ የሚፈጠረው ጥላቻ የባሰ ነው። በእርግጥ በሰለጠኑት አገራት፣ የፍቺ ጣጣዎችን በስርዓት ለማስኬድና የመናቆር ስሜቶችን ለማብረድ፣ ባልና ሚስት የህግ ባለሙያዎችን (ጠበቆችን) ይዘው ነው የሚከራከሩት ወይም የሚደራደሩት። ግን፣ ይሄም ቢሆን ወጪው ቀላል አይደለም። አሜሪካ ውስጥ፣ በፍቺ የሚለያዩ ጥንዶች፣ እያንዳንዳቸው በአማካይ 10 ሺ ዶላር ለህግ አማካሪ ይከፍላሉ። አንድ ትዳር ሲፈርስ 20 ሺ ዶላር ለጠበቆች ክፍያ ይውላል ማለት ነው። ሌሎች ወጪዎች ተጨምረውበት፣ በአሜሪካ የፍቺ ነገር በአመት 30 ቢሊዮን ዶላር ገደማ እንደሚፈጅ፣ ሰሞኑን የወጣው የፎርብስ መፅሄት ገልጿል።

ምን ያህል ሰው በዚህ ወጪ እንደሚቸገር አስቡት። የቢዝነስ ስራ ዋነኛ ባህርይ፣ “ችግሮችን የሚያቃልልና ወጪዎችን የሚቀንስ መፍትሄ” ማቅረብ አይደል? ይሄውና፣ የ37 አመቷ ሚቸል ክሮዝቢ፣ የፍቺ ወጪዎችን በሶስት እጅ የሚቀንስ ዘዴ በመፍጠር የቢዝነስ ስራ ጀምራለች። ጥንዶች ለፍቺ ከሃያ ሺ ዶላር በላይ ማውጣት አይኖርባቸውም። ከ7ሺ ዶላር ባነሰ ወጪ ጉዳያቸውን በድርድር ይጨርሳሉ። በዚያ ላይ ደግሞ፣ ከተጨማሪ ቂምና ጥላቻ ይድናሉ የምትለው ክሮዝቢ፣ በቢዝነሷ ስኬታማ በመሆኗ ባለፉት ጥቂት ወራት ድርጅቷ አንድ ሚሊዮን ዶላር ገቢ አግኝቷል - ፎርብስ እንደዘገበው።

መቼስ፣ ፍቺ ከተፈፀመ አይቀር፣ ወጪንና ጥላቻን የማያባብስ ዘዴ ሲገኝለት መልካም ነው። በአሜሪካ ከጊዜ ወደ ጊዜ ጋብቻና ፍቺ የሚፈፅሙ ሰዎች ከጠቅላላ የህዝብ ቁጥር ጋር ሲነፃፀሩ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀነሱ መጥተዋል። ከሃያ አመት በፊት፣ ከአስር ሺ ሰዎች መካከል በአመት 98 ጋብቻዎች እና 47 ፍቺዎች ይፈፀሙ ነበር። ዛሬ የጋብቻዎቹ ቁጥር ወደ 68፣ የፍቺዎቹ ቁጥር ደግሞ ወደ 34 ቀንሷል። በአጠቃላይ ግን ባለፈው አመት በምድረ አሜሪካ ከ2.1 ሚሊዮን በላይ ጋብቻዎችና ወደ ዘጠኝ መቶ ሺ ገደማ ፍቺዎች ተፈፅመዋል። የአውሮፓም እንዲሁ ተመሳሳይ ነው፤ በአመት 2.2 ሚሊዮን ጋብቻዎችና አንድ ሚሊዮን ገደማ ፍቺዎች ይፈፀማሉ።

በፖለቲካ ግጭትና በገንዘብ እጥረት ሳቢያ የተጓተተው የዚምባብዌ ምርጫ፣ በደቡብ አፍሪካ ሸምጋይነትና በ100 ሚሊዮን ዶላር እርዳታ እርዳታ ቢታገዝም፣ እንደገና ከመራዘም አለመዳኑን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል። ለሰኔ ወር ታስቦ የነበረው ምርጫ፣ ወደ ሐምሌ፣ ከዚያም ወደ መጪው ጥቅምት ወር ተሸጋግሯል። በአልማዝ ማዕድን፣ በብረት ምርት፣ በእህል ኤክስፖርትና በሌሎች ጠንካራ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች ትታወቅ የነበረችው አገር፣ እንጦሮጦስ የወረደችው በጥቂት አመታት ውስጥ ነው። ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ የሚመሩት መንግስት፣ የግለሰቦችን ንብረት እየወረሰና አለቅጥ ገንዘብ እያተመ፣ በ10 አመታት ውስጥ አገሪቱን የረሃብና የስራ አጥነት መናኸሪያ አድርጓቷል። የራሷ የገንዘብ ኖት የሌላትና ምርጫ ማካሄድ የማትችል የቀውስ መንደር የሆነችው ዚምባብዌ እንደአወዳደቋ በፍጥነት፣ ቶሎ ልታገግም ትችላለች ተብሎ አይታሰብም።

ዚምባብዌ፣ እንደ ሶማሊያ ወይም እንደ ኮንጎ በለየለት ጦርነት ውስጥ ሳትዘፈቅ፤ “በመንግስት ጥረት በአጭር ጊዜ ውስጥ የሾቀች አገር” በመሆኗ ከሌሎች የአፍሪካ አገራት ለየት የምትል ትመስላለች። ለዚህም ነው፣ የአውሮፓ አገራትና አሜሪካ በሙጋቤ መንግስት ላይ፣ የተለያዩ ማዕቀቦችን የጣሉት። ነገር ግን፣ የመጠንና የደረጃ ጉዳይ ካልሆነ በቀር፣ ዚምባብዌ ከሌሎች የአፍሪካ አገራት ብዙም አትለይም። እጅግ ገዝፈውና ገንነው የሚታዩት የዚምባብዌ ሁለት ዋና ዋና ችግሮች…፣ ያው በሌሎች የአፍሪካ አገራትም ዘወትር የሚታዩ ችግሮች ናቸው። በአንድ በኩል፣ በፖለቲካ አፈናና ግጭት የምትናጥ አገር ነች - እንደ ብዙዎቹ የአፍሪካ አገራት። በሌላ በኩል ደግሞ የግል ቢዝነስን እንደ ጠላት የሚፈርጅ መንግስት፣ አለቅጥ ገንዘብ ማተምንና የውጭ እርዳታን የለመደ ነው - ይሄም በበርካታ የአፍሪካ አገራት የሚታይ ችግር ነው። የኬቶ ኢንስቲቱይት ጥናት እንደሚያመለክተው፣ የዚምባብዌ መንግስት በየአመቱ ብዙ የገንዘብ ኖት የማተም አባዜው እየተባባሰ የመጣው የዛሬ 15 አመት ገደማ ነው።

ከዚያም በፊት ቢሆን፣ ከልክ ባለፈ የገንዘብ ህትመት ሳቢያ “የዚምባብዌ ዶላር” ቀስ በቀስ ዋጋ እያጣ ነበር። በየአመቱ የሸቀጦች ዋጋ ከአስር እስከ ሃያ በመቶ እየናረ ቆይቷልና። በኢትዮጵያና በሌሎቹ የአፍሪካ አገራት በየጊዜው ከሚታየው የዋጋ ንረት አይለይም። እ.ኤ.አ ከ1998 በኋላ ግን፣ የገንዘብ ህትመቱ ይበልጥ እየጨመረ መጣ። እናም፣ ሃያ በመቶ የነበረው አመታዊ የዋጋ ንረት፣ ወደ 48% ዘለለ። መንግስት የገንዘብ ህትመቱን አደብ ሊያስገዛ ባለመፈለጉ፣ በቀጣዩ አመት የዋጋ ንረቱ ባሰበት - ወደ 60% ተጠጋ። እንደእብደት ሊቆጠር ይችላል። ግን፣ በአገራችንም ሚሊዬነሙ መባቻና የዛሬ ሁለት አመት የታየው የዋጋ ንረት፣ ስድሳ እና አርባ በመቶ ገደማ የደረሰ እንደነበር አስታውሱ። በእሳት መጫወት ይሉሃል ይሄ ነው! ለምን ቢባል፣ የገንዘብ ህትመት በጊዜ ካልተገታ፣ አብዛኛው ሰው በአገሬው ገንዘብ ላይ እምነት እያጣ፣ የዋጋ ንረት ከቁጥጥር ውጭ ይሆናል።

በዚምባብዌ ለሶስተኛ አመት ከሃምሳ በመቶ በላይ የሆነ የዋጋ ንረት ከተመዘገበ በኋላ ነው ነገር የተበላሸው። በ2001 የዋጋ ንረት ከእጥፍ ላይ በማሻቀቡ ኢኮኖሚው ተመሳቀለ። ከዚህ በኋላ መንግስት ሊቆጣጠረው አልቻለም። አዙሪት ውስጥ እንደመግባት ነው። በገንዘብ ህትመት የተነሳ ዋጋ ይንራል። በዋጋ ንረት ሳቢያ የመንግስት ወጪ ያሻቅባል። ወጪውን ለመሸፈን ገንዘብ ስለሚያትም የዋጋ ንረቱ ይባባሳል። በዚህ አዙሪት ውስጥ የገባው መንግስት፣ በዚያው አመት ለመጀመሪያ ጊዜ ባለ አምስት መቶ ኖት አሳተመ። በቀጣዩ አመት የዋጋ ንረት በእጥፍ ጨመረና 200% ደረሰ። መንግስት ባለ አንድ ሺ ኖት አሳተመ። የዋጋ ንረት ወደ 600% ተወረወረ። አንዴ ከቁጥጥር ውጭ ከሆነ በኋላ፣ እንደ ገና ወደ ጤንነት ለመመለስ ዳገት ነው። ያኔ፣ መንግስት ባለ 5ሺ፣ ከዚያ ባለ10ሺ፣ ከዚያም ባለ20ሺ ኖት አሳተመ - በሶስት ወራት ልዩነት። ትንሽ ቆይቶ ደግሞ ባለ ሃምሳ ሺ! የመቶ ሺ ኖት በታተመበት በ2006፣ የሸቀጦች ዋጋ በአመት ውስጥ በ12 እጥፍ ጨመረ። በ1998 ከነበረው የሸቀጦች ዋጋ ጋር ከተነፃፀረማ፣ የትየለሌ ነው። አንድ የዚምባብዌ ዶላር ይሸጥ የነበረው ክብሪት፣ ዋጋው ወደ ሰላሳ ሺ አሻቅቧል። በዚህ አላቆመም።

በቀጣዩ አመት መንግስት ባለ “ሁለት መቶ ሺ ኖት” ማሳተም ጀመረ። በወር ልዩነት የሩብ ሚሊዮን እና የግማሽ ሚሊዮን ኖቶች በገፍ ታተሙ። የዋጋ ንረት በአንድ አመት ውስጥ በስድስት መቶ እጥፍ ጨመረ። የዚምባብዌ መንግስት የ2008 አዲስ አመትን የተቀበለው ባለ ሚሊዮን ኖት በማሳተም ነው። ከዚያማ ተዉት። ወር ሳይሞላው ባለ አምስትና ባለ አስር ሚሊዮን ኖቶችን አምጥቶ አገሬው ላይ አራገፈው። ሁለት ወር ቆይቶ፣ በባለ 25 እና በባለ 50 ሚሊዮን ኖቶች አገር ምድሩን አጥለቀለቀው። አመቱ ሳይጋመስ፣ የመቶ ሚሊዮንና የአምስት መቶ ሚሊዮን ኖቶች ከታተሙ በኋላ፣ ባለ ቢሊዮን ኖት መጣ። አገር ጉድ አለ። የ25 እና የ50 ቢሊዮን ኖቶች እየታተሙ መሆናቸው አልታወቀም ነበር። የመቶ ቢሊዮን ኖት ደረሰ። በዚህ ወቅት “የዋጋ ንረት የት ደረሰ?” ብሎ ለማስላት መሞከር በጣም ከባድ ሆኗል - የሸቀጦች ዋጋ በየሰዓቱ ስለሚንር። የትሪሊዮን ኖቶች የመጡት በአዲስ አመት ነው - በ2009። በአመቱ የመጀመሪያው ወር ላይ፣ ዚምባብዌ የአለም ሪከርድ ሰበረች።

እስከዚያው ድረስ በአለማችን ከተመዘገቡት የዋጋ ንረት እብደቶች ሁሉ የባሰና፣ 14 ዜሮዎች የተደረደሩበት ባለ መቶ ትሪሊዮን ኖት አሳተመች። ግን ዋጋ የለውም። አንድ ሺ ያህል ባለ መቶ ትሪሊዮን ኖቶች ይዞ፣ አንዲት ዳቦ መግዛት አይቻልም። አብዛኛው ሰው፣ የአገሬውን ገንዘብ መጠቀም አቁሟል። በውጭ ምንዛሬ መገበያየት በአዋጅ ቢከለከልም፣ ሰዉ ሁሉ በዶላርና በዩሮ ብቻ የሚጠቀም ሆኗል። ምንም ማድረግ ስላልተቻለ፣ ከዚያን ጊዜ ወዲህ መንግስትም በዶላርና በዩሮ መጠቀም ጀመረ።

አገሪቱ ከዚያን ጊዜ ወዲህ የራሷ ገንዘብ የላትም። አዲስ አመትን በአዲስ የገንዘብ ህትመት መቀበል የለመደው የዚምባብዌ መንግስት፣ የእንጦሮጦስ ጉዞውን መቀጠል አልቻለም። እናም ዘንድሮ፣ በአዲስ አመት የመንግስት ካዝና ውስጥ የነበረው ገንዘብ 217 ዶላር ብቻ ነበር። ምርጫ ለማካሄድ መቶ ሚሊዮን ዶላር ከየት ይምጣ? እርዳታ ነዋ። አገሪቷ ግን በአልማዝ ማዕድን ከበለፀጉት የአለማችን አገራት መካከል አንዷ ነች። ነገር ግን፤ ኢኮኖሚን ለማቃወስ “የሚተጋ” መንግስት ባለበት አገር፣ መስራትና ማምረት ከባድ ነው። ከተመረተም፣ የዝርፊያና የሙስና ሲሳይ ነው የሚሆነው።

Cervical cancer… የማህጸን በር ካንሰር ...80% ያህል በታዳጊ አገሮች ይከሰታል

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፣የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር እና ጀርመን የሚገኘው ማርቲን ሉተር ዩኒቨርሲቲ በኢትዮጵያ የማህጸን በር ካንሰርን ለመከላከል የሚያስችል ፕሮጀክት ተግባራዊ ለማድረግ በአዲስ አበባ ስብሰባ አካሂደዋል፡፡ እንደአውሮፓውያኑ የጊዜ ቀመር 10/4/2013 ማለትም ሚያዝያ 2/2005 በኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር የስብሰባ አዳራሽ በተካሄደው ስብሰባ በጋራ አብረው ለመስራት የታሰቡት ድርጅቶች ተወካዮችና ከኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስርም እንግዶች ተገኝተው ነበር፡፡ ዶ/ር ተናኘ ጸጥአርጌ ከኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስር ስብሰባውን ሲከፍቱ እንደተናገሩት በኢትዮጵያ ከስነተዋልዶ ጤና ጋር በተያያዘ ለሴቶች ሞት በምክንያትነት ከሚጠቀሱት የማህጸን በር ካንሰር ይገኝበታል፡፡

ይህ በሽታ በብዙ ሴቶች ላይ የሚከሰትና በአስከፊነቱም በቀዳሚነት የተመዘገበ ነው፡፡ ማንኛዋም የግብረስጋ ግንኙነት የምትፈጽም ሴት በበሽታው ለመጠቃት እንደምትችል መረጃዎች እንደሚጠቁሙ ዶ/ር ተናኘ ተናግረዋል፡፡ ዶ/ር ካሳሁን ኪሮስ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስትና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሜዲካል ፋኩልቲ በአንድ ወቅት እንደገለጹት የማህጸን ካንሰር አይነቱ ብዙ ሲሆን በአገራችን በብዛት የሚያጠቃውና ገዳይ የሆነው የማህጸን በር ካንሰር (Human Papiloma Virus) ሒዩማን ፓፒሎማ በተባለው ቫይረስ አማካኝነት የሚከሰተው ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ለማህጸን በር ካንሰር መከላከያ የሚሆኑ ሁለት አይነት ክትባቶች የተገኙ ሲሆን አንዱ Gardasil ሲሆን ሁለተኛው Cervarix የተሰኘው ነው፡፡ Gardasil K Human Papiloma Virus ለማህጸን በር ካንሰር መንስኤ ለሆነው መከላከያ ክትባት ሲሆን አራት የቫይረስ አይነቶችን ማለትም 16...18...6...እና 11 የተባሉትን የቫይረስ አይነቶች የሚከላከል ነው፡፡ በተመሳሳይም Cervarix የተባለው ክትባት 16...እና...18 የተባሉትን ቫይረሶችን ብቻ የሚከላከል የክትባት አይነት ነው፡፡ የማህጸን በር ካንሰር 70 ኀያህሉ የሚከሰተው በእነዚህ በ16 እና 18 በተባሉ የቫይረስ አይነቶች መሆኑ ተረጋግጦአል፡፡

በዓለማችን በየሁለት ደቂቃ አንድ ሴት በየሰአቱ ደግሞ ሰላሳ ሴቶች በማህጸን በር ካንሰር ምክንያት ለህልፈት ይዳረጋሉ፡፡ በዓለም አሀዝ መሰረት በየአመቱ እስከ ግማሽ ሚሊዮን ሴቶች የማህጸን በር ካንሰር ያላቸው መሆኑን በምርመራ የሚያረጋግጡ ሲሆን ከእነዚህም እስከ ሁለት መቶ ሰባ አምስት ሺህ የሚሆኑት በዚሁ ህመም ምክንያት ሕይወታቸው ያልፋል፡፡ ዶ/ር ተናኝ ጸጥአርጌ ከኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስር እንደገለጹት በብሄራዊ ደረጃ በየአመቱ ወደ 7619/ ሰባት ሺህ ስድስት መቶ አስራ ዘጠኝ ሴቶች በማህጸን በር ካንሰር ሊያዙ እንደሚችሉና ከነዚህም ወደ 6081/ ስድስት ሺህ ሰማንያ አንድ የሚሆኑት ለህልፈት እንደሚዳረጉ ይገመታል፡፡ ይህ ቁጥር የሚያሳየው ምን ያክል ታማሚዎች እንዳሉና የሞት ቁጥሩም ቀላል እንዳልሆነ ሲሆን በተያያዠነትም ለጉዳዩ የተሰጠው ትኩረት ምን ያህል እንደሆነ እንዲሁም አገልግሎቱ መስፋፋት እንዳለበትም የሚጠቁም ነው፡፡

የኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስር በብሕራዊ ደረጃ ወደ 118/የሚሆኑ የጤና ተቋማት የማህጸን በር ካንሰርን በሚመለከት ትኩረት ሰጥተው እንዲሰሩ የሚያስችል አሰራር በመዘርጋት ላይ ነው፡፡ ስለዚህም ይህንን በሽታ ለመከላከል በቂ የሆነ የህክምና አገልግሎት መሰጠት በምእተ አመቱ የልማት ግብ ከታቀዱት መካከል የእናቶችን ሞት ለመቀነስ ይረዳል፡፡ እስከአሁን ባለው አሰራር ለ2015/ የታቀደውን የልማት ግብ ለማሳካት ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ እና ውጤት የሚያስመዘግቡ ስራዎች እየታዩ ቢሆንም አሁንም ገና ብዙ መሰራት እንዳለበት ከሚጠቁሙት እውነታዎች መ..ከል የማህጸን በር ካንሰር ይኝበታል፡፡ ይህም በብሕራዊ ደረጃ ከታቀደው የስነተዋልዶ አካላት ጤና አጠበባበቅ ጋር የሚገናኝ ነው ብለዋል ዶ/ር ተናኘ፡፡ ዶ/ር ይርጉ ገ/ሕይወት የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት በአ.አ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ፋክልቲ መምህር እና የኢሶግ ፕሬዝዳንት በትብብር መስራትን በሚመለከት በሰጡት ማብራሪያ .. ...እንደሚታወቀው በአብዛኛው ትኩረት የሚሰጠው አጣዳፊ ለሆኑት እና ተላላፊ በሽታዎች ቢሆንም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ይህ አዝማሚያ እየተለወጠ ሌሎች ከሰው ሰው በቀላሉ የማይተላለፉ ነገር ግን ሕይወትን አደጋ ላይ የሚጥሉ የጤና ችግሮችም ትኩረት እያገኙ በመምጣት ላይ ናቸው፡፡

ለምሳሌ..የውስጥ አካላት ሕመሞች...የደም ግፊት...የስኩዋር ሕመም የመሳሰሉት ከሰው ሰው በመተላለፍ ጉዳት የማያስከትሉ ቢሆንም ሰዎችን ግን ጤናቸውን የሚያቃውሱ በመሆኑ በአለም አቀፍ ደረጃ አትኩሮትን ያገኙ ናቸው፡፡ በዚሁ ረገድም ከስነተዋልዶ አካላት ጋር ተያይዘው የሚገኙ የተለያዩ የካንሰር አይነቶችን በሚመለከት የበለጠ ግንዛቤ የሚገኝበት የችግሩም ስፋት የሚታወቅባቸው መድረኮች እየተፈጠሩ ነው፡፡ የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር አባላት አብዛኞቹ በቀጥታ ከጽንስና ማህጸን ሕክምና ጋር የተያያዘ የህክምና አገልግሎት የሚሰጡ እንደመሆናቸው ታማሚዎችን በህክምናው አገልግሎት የመርዳት ስራ ይሰራሉ፡፡ በዚህም እንደሚታየው አብዛኞቹ የማህጸን በር ካንሰር ታማሚዎች ወደህክምናው የሚመጡት በሽታው ስር ከሰደደና ከተሰራጨ በሁዋላ በመሆኑ በቀላሉ ለማከምና ለማዳን እጅግ ፈታኝ ሁኔታዎች ይገጥማሉ፡፡ ስለዚህ ይህንን ሁኔታ ለመለወጥ ምን ማድረግ ያስፈልጋል የሚለውን ለመነጋገር የተፈጠረው የምክክር መድረክወደ ሶስት ነገሮችን ማድረግ እንደሚቻል አሳይቶአል፡፡

ግንዛቤ የማስጨበጥ ስራ መስራት ... ሴቶች በችግሩ ስር በሰደደ እና በከፋ ሁኔታ ከመጠቃታቸው በፊት ሊታከሙ በሚችሉበት የህክምና ተቋም በመሄድ ሕክምና እንዲያደርጉ ያስችላል የሚል ግምት አለ፡፡ የችግሩን ስፋትና ጥልቀት ማወቅና የዚያኑ ያህል ተመጣጣኝ የሆኑ እንቅስቃሴ ዎችን ማድረግ አስፈላጊ በመሆኑ አንዳንድ የዳሰሳ ጥናቶችን ማድረግ፣ይህም የሚሰሩ ስራዎች በትክክለኛ መረጃ ላይ የተመሰረተ ከሆነ የተጀመረውን ፣ መሰራት የሚገባውንና ከአመታት በሁወላ ሊደረስበት የሚገባውን ደረጃ ለማወቅ ይረዳል፡፡ ቅድመ ካንሰር ሁኔታውን አስቀድሞውኑም ማወቅ የሚቻልበት የህክምና አሰራሮች ስላሉ ይህንን አገልግሎት በቀላሉና በስፋት እንዴት ማዳረስ ይቻላል የሚለውን ስብሰባው ተመልክቶአል፡፡ ለዚህም ተቋሞችን በሰለጠነ የሰው ኃይል እና በተገቢው መሳሪያ ማጠናከር እና አስፈላጊው ግብአት የሚገኝበትን ሁኔታ ስብሰባው ተነጋግሮአል፡፡ የካንሰር ሕክምና እስከአሁን የሚሰጠው ውስን በሆኑ የህክምና ተቋማት በተለይም በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ሲሆን ነገር ግን የሆስፒታሉ አቅም ውስን በመሆኑ ታካሚዎች በጣም ለረጅም ጊዜ ህክምናውን ለማግኘት ወረፋ የሚጠብቁበት ሁኔታ ይታያል፡፡ ይህንን ለውጦ ተደራሽነትን ለማስፋት እንዴት ይቻላል የሚለው መልስ እንዲያገኝ ክህሎትን የማሳደግና ግብአትን የማሟላት ስራ መስራት አስፈላጊ መሆኑ ተጠቁሞአል፡፡

ይህ እቅድ ከተሳካ በሚቀጥሉት ሁለት አመታት ውስጥ ጠንካራ ስራዎችን መስራት ይቻላል ተብሎ ይታሰባል፡፡ ይህ እሳቤ እውን ከሆነ በሁዋላም የማህጸን በር ካንሰርን የመከላከል ስራ በፕሮጀክት ተይዞ የሚቀጥል ሳይሆን ከተወሰኑ የጊዜ ሂደቶች በሁዋላ እንደማንኛውም መሰረታዊ የጤና ሁኔታ ተይዞ በአገር አቀፍ ደረጃ በተሙዋላ አገልግሎቱን መስጠት ይቻላል የሚል እምነት አለ፡፡ የካንሰር ህክምና በሶስት ደረጃ ተመጣጥኖ የሚሰጥ ነው፡፡ እሱም የጨረር ፣የቀዶ ሕክምና እና በመድሀኒት የሚሰጥ በመሆኑ ከፍተኛ ወጪን የሚጠይቅ ነው፡፡ አሰጣጡም ለየትኛው ታማሚ ምን አይነት ሕክምና ያስፈልገዋል የሚለው በምርመራ አማካኝነት የሚወሰን ሲሆን ወጪው ለምርመራ የሚረዱ መሳሪያዎችን ከማሟላት አንጻር ብቻ ሳይሆን የሙያተኞች እና የሚወሰዱ መድሀኒቶችን ጭምር ያካትታል፡፡ የምርመራ መሳሪያዎችን ሁኔታ ስንመለከት ደግሞ እጅግ ዘመናዊ የሆኑ መሳሪያዎች በአለም ገበያ ላይ የሚገኙ ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ ዋጋቸው ተመጣጣኝ የሆነ ብዙ ሰዎችን ለመርዳት የሚያስችሉም አሉ፡፡ ስለዚህ በከፍተኛ ደረጃ የሚገኘውን የክኖሎጂ ውጤት የምንጠብቅ ከሆነ አቅምም ስለማይፈቅድ ተጠቃሚ የሚሆኑትም ውስን ተቋማት ናቸው፡፡

ዝቅተኛ ወጪ የሚያስወጡ አማራጭ የምርመራ ዘዴዎችን የምንጠቀም ከሆነ ግን አሰራሩን በስፋት እስከጤና ጣቢያ ድረስ መዘርጋት የሚያስችል ሁኔታ ይፈጠራል፡፡ በአገራችን ያለውን የእናቶች ሞት መጠን ለመቀነስ እንዲያስችል አገልግሎቱን በስፋት ማዳረስ አማራጭ የሌለው አሰራር መሆኑን አምኖ በተመጣጣኝ ዋጋ በስፋት ሊዳረስ የሚችለውን መሳሪያ እና ግብአት ወደሀገር በማስገባት የብዙ ሴቶችን ሕይወት ማትረፍ ተገቢ ነው በሚል ከስምምነት የተደረሰበት ነበር የጋራ ምክክሩ ብለዋል ዶ/ር ይርጉ ገ/ሕይወት የኢሶግ ፕሬዝዳንት፡፡ ማንኛዋም ሴት በተለይም እድሜዋ ከሰላሳ አመት በላይ ከሆነ ቢቻል በየአመቱ ባይቻል በየሶስት አመቱ አለበለዚያም በየአምስት አመቱ የቅድመ ካንሰር ምርመራ ብታደርግ ካንሰርን አስቀድሞ መከላከል ይቻላል፡፡ መጥፎ ጠረን ያለው የማህጸን ፈሳሽ ከግብረስጋ ግንኙነት በሁዋላ ወይንም ብልትን በማጽዳት ወቅት እንዲሁም ሰውነት በመንካት ወቅት ደም መፍሰስ ካሳየ ወዲያውኑ ወደሐኪም ሄዶ መፍትሔ ማግኘት ይቻላል፡፡