Administrator

Administrator

  • ፓትርያሪክ እንድሆን የመንግስት ባለሥልጣን አላግባባሁም 
  • ‹ካህናትና ምእመናን ለቤተ ክርስቲያንና ለቤተ ክርስቲያን ብለው ብቻ ማሰብ፣ ይገባቸዋል›› - /ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል/

አምስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ የነበሩት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በሞተ ሥጋ ከተለዩ ስድስት ወራት ተቆጠሩ፡፡ ከፓትርያርኩ ኅልፈት በኋላ በሕገ ቤተ ክርስቲያን በተደነገገው መሠረት ስድስተኛው ፓትርያርክ እስኪመረጥ ድረስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል በዐቃቤ መንበረ ፓትርያሪክነት ተሠይመው ቤተ ክርስቲያኒቱን በማገልገል ላይ ናቸው፡፡
የስድስተኛውን ፓትርያሪክ ምርጫ ለማስፈጸም ታኅሣሥ 10 ቀን 2005 ዓ.ም በቅዱስ ሲኖዶስ የተቋቋመው የፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴ ጥር 30 ቀን 2005 ዓ.ም ለብዙኀን መገናኛ ይፋ ባደረገው የምርጫ መርሐ ግብር መሠረት፤ ከየካቲት 9 - 14 ቀን 2005 ዓ.ም አምስት ዕጩ ፓትርያሪኮች ሲመርጥና ሲያጣራ ቆይቶ በዛሬው ዕለት ለቅዱስ ሲኖዶሱ እንደሚያርቀርብ ታውቋል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤም ከዛሬ ጀምሮ በሚያካሂደው ውይይት የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም ለሚከናወነው ምርጫ በዕጩነት በሚቀርቡት አምስት ዕጩ ፓትርያሪኮች ላይ የመጨረሻ ውሳኔ አሳልፎ የዕጩዎቹን ዝርዝር ይፋ እንደሚያደርግ ይጠበቃል፡፡
የምርጫው ሂደት በይፋ ከተጀመረ አንሥቶና ከዚያም በፊት ቀጣዩ ፓትርያሪክ እንደሚኾኑ ብዙ ከተነገረላቸው ሊቃነ ጳጳሳት መካከል የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል አንዱ ናቸው፡፡ ብፁዕነታቸው በፓትርያሪክነት ምርጫው ከሚሳተፉ ከ800 በላይ መራጮች የምርጫ ድጋፍ ለማሰባሰብ በሥልጠና ስም በርካታ ገንዘብ ማውጣታቸውን፤ በሕንፃ ኪራይ፣ በሥራ ምደባ፣ በውጭ ተልእኮና በሹመት አሰጣጥ ለብዙዎች ቃል መግባታቸውን፤ ከዚህም አልፎ ቀጣዩ ፓትርያሪክ እርሳቸው እንደሚኾኑ ራሳቸውን ለመንግሥት አካላት ስለ ማስተዋወቀቸው በአንዳንድ ሚዲያዎች ተዘግቧል፡፡
በእኒህ ጉዳዮች ላይ የብፁዕ አቡነ ሳሙኤልን አስተያየት ከራሳቸው አንደበት ለመስማት የአዲስ አድማስ ሪፖርተር ሰላም ገረመው ከብፁዕነታቸው ጋር አጭር አጠር ያለ ቆይታ አድርጋለች፡፡

በያዝነው ዓመት በኮሚሽኑ ድጋፍ ለአህጉረ ስብከት ሓላፊዎች የተሰጡ ሥልጠናዎች፣ በአዲስ አበባ ከግብጽ ቤተ ክርስቲያን ጋር የተደረጉ የልምድ ልውውጦች ከፓትርያሪክ ምርጫው ጋር በተያያዘ ለብፁዕነትዎ ድጋፍን የመሸመት ዓላማ እንደነበራቸው ይነገራል፡፡ የተሰጠው ሥልጠና ምን ነበር? ዓላማውና የበጀት ምንጩስ?
ከግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከመጡ ልኡካን ጋር የተደረገው የልምድ ልውውጥና የተሰጠው ሥልጠና፣ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከግብጹ ፖፕ አቡነ ሺኖዳ ጋር ቀድሞ በደረሱበት ስምምነት መሠረት የተፈጸመ፣ ነገር ግን ዘግይቶ የተፈጸመ ስለኾነ እንጂ ከፓትርያሪኩ ኅልፈት በኋላ የታቀደና ለምርጫ ድጋፍ ቅሰቀሳ የታሰበ አይደለም፤ በቀጣይም ከሌሎች አኀት አብያተ ክርስቲያናት ለምሳሌ ከሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጋር በተመሳሳይ መድረኮች የመገናኘት ዕቅድ አለን፡፡
ለአህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆችና ሌሎች ሓላፊዎች በጥቅምት ወር ከሀገር አቀፉ አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ጋር ተያይዞ የተሰጠው ሥልጠና አምናም በተመሳሳይ ወቅት የነበረ ነው፡፡ በ2004 ዓ.ም ጥቅምት ወር ፓዝፋይንደር ኢትዮጵያ በሰጠው የገንዘብ ድጋፍ በሥነ ተዋልዶና የሴት ልጅ ግርዛት ላይ ያተኮረ ሥልጠና ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና ለአህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች ተሰጥቷል፡፡

በዚህ ዓመት ‹‹ዳቦ ለዓለም›› በተባለ ገባሬ ሠናይ ድርጅት ድጋፍ በአቅምና የሰላም ግንባታ ጭብጥ ዙሪያ በታቀዱ በርካታ ርእሰ ጉዳዮች ላይ በመስኩ ባለሞያዎች ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡ ዋና ዓላማው በቤተ ክርስቲያናችን መልካም አስተዳደር እንዲጠናከር፣ ፍትሕ እንዲሰፍንና የልማት አቅም እንዲፈጠር ነው፡፡ ስለዚህ ምርጫው ስላለ ወይም ከምርጫው ጋር ተያይዞ የታቀደ ነገር አይደለም ማለት ነው፡፡ 
ለሥልጠናው ተሳታፊዎች በአበል መልክ እንደተጨማሪ ክፍያ ወጥቷል የተባለው 500,000 ብርና የበጀት ምንጩስ?
የዚህ ዓመት ሥልጠና የበጀት ምንጩ እንደተናርኹት እኛው ቀርጸን ለ‹‹ዳቦ ለዓለም›› (Bread For the World) ገባሬ ሠናይ ድርጅት ባቀረብነው ፕሮፖዛል መሠረት የተገኘ ገንዘብ ነው ለሥልጠናው ማስፈጸሚያና ለአበል የተከፈለው፡፡ ይህም በየዓመቱ በተለያዩ ርእሰ ጉዳዮች ላይ ፕሮፖዛል እየቀረጽን፣ ድጋፍ ሰጪ ድርጅቶችን እየጠየቅን ስንሠራው የቆየና ለወደፊቱም የሚቀጥል ነው፡፡ ለሥልጠናው ወጭ የተደረገው ገንዘብ ለአፋርና ለሶማሌ ክልሎች ለሚሠሩ የልማት ፕሮጀክቶች የተገኘ ገንዘብ ነበር ለተባለው በክልሎቹ ለምንሠራው ሥራ ድጋፍ ያገኘነው ከተመድ የስደተኞች ማእከል (UNCR) ነው፤ ገንዘቡንም የሚቆጣጠረው ራሱ ማእከሉ ነው፡፡ ስለዚህ ከሥልጠናው ወጪ ጋር አይገናኝም፡፡
ከምርጫው ጋር በተያያዘ÷ ሹመት እንደሚሰጣቸው፣ በሥራ እንደሚመደቡ፣ በሕንጻ ኪራይ፣ በውጭ ዕድል ቃል የተገባላቸው መራጮች አሉ ተብሏል…
ለመሾምም፣ ሕንጻ ለማከራየትም፣ በሥራ ለመመደብም፣ ወደ ውጭ ለመላክም ሥርዐት አለው፡፡ ከተጠቀሱት የትኛውም ነገር ከሥርዐት ውጭ እንዳይፈጸም ተከፍቶ የነበረው መንገድ ተዘግቷል፡፡
በሌላ በኩል የፓትርያሪክ ምርጫ መንፈሳዊ ጉዳይ ነው፡፡ በዚህ መንገድ ፕትርክናውን ለማግኘት ማሰብና መሞከር ሕግም አይፈቅድም፡፡ ይህ የሥልጣን ስግብግብነት ነው፡፡ መራጮቹስ እነማን እንደኾኑ በስም ይታወቃሉ ወይ? ይህን አሉባልታ ያመነጩትና የሚያስተጋቡት የምርጫውን ሂደት ለማወናበድ፣ ሕጋዊውን አሠራር ወደ ቤተሰባዊነት፣ ዘረኝነትና አድሏዊነት ለመውሰድ ማመኻኛ የሚሹ ሕገ ወጥ ቡድኖች ናቸው፡፡
ስድስተኛው ፓትርያሪክ ኾነው እንዲመረጡ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን፣ የቤተ ክህነት አመራሮችንና ታዋቂ ግለሰቦችን አግባብተዋል? ስለጉዳዩ ላይ ሊቃነ ጳጳሳቱ ትችት እንደሰጡ ተዘግቧል።
ምረጡኝ ብዬ አላልኹም፤ ምረጡኝ ብዬ አላውቅም፡፡ ይህን አድርገኻል የሚሉኝ ወገኖች እውነተኛ ከኾኑ መረጃውን ለምን አያቀርቡም? የቤቱን [የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን] ዕድገት፣ ልማትና መሻሻል ርምጃዎች ሲያኮላሹ የነበሩ ሰዎች ስሜት ነው፡፡
የመንግሥት ባለሥልጣናትን ማግባባትዎና ‹‹መንግሥት ፓትርያሪክ ኾኜ እንድመረጥ ይፈልጋል›› እያሉ ማስወራትዎ. . .
ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮኻል፤ በየትኛውም አቅጣጫ የተለያዩ አካላት ብዙ ሊናገሩ ይችላሉ፤ ይህንንም የሚሉት የቤታችንን የዕድገትና ልማት ርምጃ ሲያኮላሹ የነበሩ ግለሰቦችና አሁን ደግሞ በምርጫው ዙሪያ የተደራጁ ቡድኖች ናቸው፡፡
ፓትርያርክነት የአባትነት፣ የቡራኬ ሥልጣን ነው፤ ለእኔ አገልጋይነት ይሻለኛል፤ አገልጋይ መኾን ነው እንጂ፤ አገልጋይነት÷ ሃይማኖትን መጠበቅና ማስጠበቅ፣ ሕዝብንና እግዚአብሔርን በማእከል ኾኖ ማገናኘት እንጂ አዛዥ፣ ገዥ፣ አሳሪ፣ አሳሳሪ መኾን አይደለም፡፡
ለመኾኑ እንዴት ነው የፓትርያሪክነት ሥልጣን ይሰጠኝ ብዬ የምጠይቀው? ሹመቱ የመንፈስ ቅዱስ ምርጫ ነው፤ ሥርዐቱ የሚፈጸመው በፍትሕ መንፈሳዊ፣ በሕገ ቤተ ክርስቲያን፣ በፓትርያርክ ምርጫ ሕገ ደንቡ መሠረት ነው፤ ሕጉን፣ ሥርዐቱን የሚፈጽመውና የሚያስፈጽመው ቅዱስ ሲኖዶሱና ሕዝቡ እንጂ መንግሥት አይደለም፤ በሕገ መንግሥቱ የመንግሥትና ሃይማኖት ግንኙነት ምን መኾን እንደሚገባው በግልጽ ተደንግጓል፡፡ ያግባባኹትም የጠየቅኹትም የመንግሥት አካል ይኹን ባለሥልጣን የለም፡፡
በምርጫው የሚሳተፉ ካህናትና ምእመናን ለሚኖራቸው ድርሻ እርስዎ ምን ይላሉ? በምርጫው ዙሪያ ይካሄዳል ስለሚባለው የቡድኖች እንቅስቃሴስ?
በየብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱ ቤት፣ በእኔም ቤት ሳይቀር እየዞሩ እገሌን ካልመረጣችኹ፣ ካላስመረጣችኹ የሚሉ አካላት እንዳሉ ግልጽ ነው፡፡ ሥልጣን ባለው አካል መንፈሳዊ ሥልጣንን ለመያዝ የሚደረገው ሽር ጉድ ሁሉ በፍትሕ መንፈሳዊ፣ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን የተወገዘ ነው፤ ይህን የሚያደርጉ አካላት በሰውና በእግዚአብሔር ዘንድ ይጠየቃሉ፡፡ እንዲህ ኾኖ የሚሾመው አባትም ቢኾን ሢመቱ ሥጋዊ ሹመት ይኾንና በነፍስም በሥጋም ያጎድለዋል፤ ያለጊዜውም ሊያሥቀስፍ ይችላል፡፡
ስለኾነም በምርጫው የሚሳተፉ ካህናትና ምእመናን ለቤተ ክርስቲያንና ለቤተ ክርስቲያን ብለው ብቻ ማሰብ፣ መወሰንና መቆም ይገባቸዋል፡፡

 

(ወ/ሮ ሙሉ ሠለሞን፤ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት)

በደርግ ዘመን በኢትዮጵያ ኢምፖርት ኤክስፖርትና የችርቻሮ ኮርፖሬሽን ውስጥ ነው ስራ የጀመሩት፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በፀሐፊነት አገልግለዋል በቢዝነስ ቢኤ ዲግሪ፣ በኢንቫይሮመንትና ዴቨሎፕመንት ማስተርስ ያላቸው ወ/ሮ ሙሉ ሰለሞን፤ አሁን ደግሞ በሊደርሺፕና ኢንተርፕሪነርሺፕ ፒኤችዲያቸውን እየሠሩ ይገኛሉ፡፡ “ራይት ቪዥን” የተባለ ኩባንያ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ የሆኑት ወ/ሮ ሙሉ፤የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማህበራት የመጀመርያዋ ሴት ፕሬዚዳንት በመሆን በማገልገል ላይ ናቸው፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ በንግስተ ሳባ ሆቴል በነበራቸው ቀጠሮ በሥራና ተመክሮ፣ በስኬትና ፈተና፣ በህይወትና ራዕያቸው ዙሪያ ያደረገችው ቃለምልልስ እንደሚከተለው ተጠናቅሯል፡፡

ለኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ፕሬዚዳንትነት ያደረጉት ውድድሩ እንዴት ነበር? 
በመሠረቱ ምክር ቤቱን ቀደም ብዬም አውቀዋለሁ፡፡ ምክንያቱም አዲስ አበባ ቻምበርን በዳይሬክተርነት አገልግያለሁ፡፡ በበጐ ፈቃደኝነት በተለያዩ ማህበራት ውስጥም ሰርቻለሁ፡፡ አሁን ደግሞ የራሴ ስራ ላይ ላተኩር ብዬ ባሰብኩበት ሰዓት ነው ወደዚህ ውድድር የገባሁት፡፡ አዲስ አበባ ቻምበር ዳይሬክተር የሆንኩት በከፍተኛ ድምጽ ተመርጬ ነው፡፡ እንደውም ፕሬዚዳንት እንድሆንም ብዙ ግፊቶች ነበሩ፡፡ ሆኖም በግሌ የምመራቸውና የምሠራቸው በርካታ ነገሮች ስለነበሩ በወቅቱ ጥያቄውን አልተቀበልኩም፡፡
የሆነ ሆኖ እኔ የአዲስ አበባ ቻምበር ዳይሬክተር ሆኜ ከ1997 ምርጫ ጋር ተያይዞ በተከሰተው ቀውስ ከሱቆች መዘጋትና ከመሳሰሉ ነገሮች ጋር በተገናኘ ፈታኝ ወቅት ነበር፡፡ ታዲያ ሱቆችን ከማስከፋት ጀምሮ አጠቃላይ የንግዱ ማህበረሰብ ወደቀድሞው መረጋጋትና የንግድ ሥርዓት እንዲገባ፣ነጋዴው በራሱ ካጠፋ እንዲጠየቅ፣ነገር ግን ድርጅቶቹ ሥራቸውን እንዲቀጥሉ የማድረግ ፈታኝ ወቅት አሳልፈናል፡፡ ያ ወቅት በጣም አስቸጋሪ ነበር፡፡
ለኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ም/ቤት የተወዳደርኩት ያለ አንዳች ተቃውሞ ሲሆን እንድወዳደር ፈርመው ነው የኔን ስም የላኩት፡፡ ነገር ግን እኔ ብዙ የራሴ ሥራ አለኝ፡፡ የአዲስ አበባውን አገልግያለሁ፡፡ ያላገለገሉ ስላሉ እነሱ ይወዳደሩ ብልም ጫናው በዛ፡፡ ምናልባት አንድም ሁለትም አመት አገልግለሽ ብትተይው ይሻላል፣ይሄ ሁሉ ሰው ያለ አንዳች ተጣባባቂ አንቺን አምኖ ሲያወዳድር እንዴት እምቢ ትያለሽ--- የሚል ጫና በረታና ተወዳደርኩኝ፡፡ በዚህ ደግሞ ሌላ ጫና ገጠመኝ፡፡
ምን ዓይነት ጫና?
ምን መሰለሽ? የበፊቱ ፕሬዚዳንት አቶ ኢየሱስ ወርቅ ዛፉ መቀጠል ይፈልጉ ነበር መሠለኝ ከየአቅጣጫው በስልክ ዛቻና ማስፈራሪያው በዛ፡፡ በአካልም መጥተው አርፈሽ ተቀመጪ፣ ቦታውን ስለሚፈልጉት ከውድድሩ ራስሽን አግልይ ያሉኝ ነበሩ፡፡ በስልክም የማላውቃቸው ሰዎች “አርፈሽ ልጆችሽን አሳድጊ” ይሉኝ ነበር፡፡ ማንነታቸውን ግን አይገልፁም፣ እኔ ደግሞ በጩኸትና በፍርሃት እንደ እያሪኮ ግንብ የምፈርስ አይነት ሰው አይደለሁም እና ጉዳዩ የበለጠ እንድፀና አደረገኝ፡፡ ለምሣሌ ሚዲያ ተቋሙንም የጋዜጠኞችንም ሥም መጥቀስ ባልፈልግም ሴት ጋዜጠኞች ማበረታታት ሲገባቸው ያቀርቡልኝ የነበረው ጥያቄ የንቀትና የማስፈራራት አይነት ነበር፡፡
እስቲ ከእርስዎ ጋር የተወዳደሩትን ሰዎች ይንገሩኝ----
ለውድድር የቀረብነው አራት ሰዎች ነን፡፡ አንደኛው ተወዳዳሪ የቀድሞው ፕሬዚዳንት አቶ ኢየሱስ ወርቅ ዛፉ ናቸው፡፡ አባልነታቸው አዲስ አበባ ቢሆንም ከአዲስ አበባ አልተወከሉም፡፡
ህጉም የሚለው ካለሽበት ክልል ተወክለሽ ነው የምትወዳዳሪው፣ካለሽበት ክልል ተወክለሽ ግን የትኛውም ክልል ሊመርጥሽ ይችላል፡፡ አቶ ኢየሱስ ወርቅ የተጠቆሙት ከሌላ ክልል ነበር፣ይህም የምርጫው ቀን ጭቅጭቅ አስነስቶ ነበር፡፡ ሌላው ጌታቸው አየነው ከአማራ ክልል ነበር፣ሶስተኛው የማላውቀው ሰው ነበር - ለውድድሩ አልቀረበም፣ እኔ አራተኛ ነኝ፡፡ ለምክትል ፕሬዚዳንትነትና ለቦርድ አባልነት የሚወዳደሩም ነበሩ፡፡ ለውድድሩ ንግግር ስናደርግ ከአማራ ክልል የመጣው ራሱን አገለለ (ሪዛይን አደረገ)፣ አንደኛው መጀመሪያውኑም አልመጣም፣ ስለዚህ እኔና አቶ ኢየሱስ ወርቅ ብቻ ቀረን፡፡ እዛ ውድድር ላይ ቀድሞ የተሠራ ሥራ እንደነበር ፍንጮች ነበሩ እናም በሻይ ሰዓት “እናንተ በቃ ሴት አትመርጡም አይደል” እያልኩ እቀላልድ ነበር፡፡
ቀደም ብሎ የተሠራው ስራ ምንድን ነው?
እሣቸውን ለመምረጥ ተማምለው የመጡ እንደነበሩ መረጃ አለኝ፣በአንደበታቸውም ይህንኑ የነገሩኝ አሉ፡፡ የሆነ ሆኖ እኔ እዚህ ተወዳድሮ በመመረጥ እንጂ በሌላ ሌላው አላምንም፣ መሆንም የለበትም፣ ስለዚህ ውድድሩ ቀጠለ፡፡ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ተጀምሮ 10፡00 ሰዓት ማለቅ የነበረበት እስከ ሌሊቱ ስድስት ሰዓት ማለቅ አልቻለም፡፡ ምክንያቱም ብዙ ጫናና ፍትጊያ ነበር፡፡ ብጥብጥ እንዲፈጠር የሚፈልጉ ሰዎችም ነበሩበት፡፡ የሆነ ሆኖ እርሳቸው ንግግር አድርገው ሲጨርሱ እኔ በተራዬ ንግግር ካደረግኩ በኋላ አብላጫው ሰው ፊቱን ወደኔ አዞረ፡፡
ድምጽ ተቆጥሮ አሸናፊው እስከሚነገር ከአንድ የማላውቃቸው የክልል ንግድ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ጋር ስናወራ “እኛ አንችን አናውቅሽም ስለዚህ የምናውቀውን ለመምረጥ ስምምነት ነበረን፡፡ ነገር ግን ንግግር ስታደርጉ ሁሉም ወዳንቺ ተገለበጠ” አሉኝ፡፡
ሌሎችም እንዲሁ ወንዶችም ሴቶችም ንግግሬን እስኪሰሙ አቋማቸው የእኒህ ሰውዬ አይነት እንደነበር ነግረውኛል፡፡ በዚህ ሁኔታ ነው ያሸነፍኩት፡፡ እኔ 132፣ እሣቸው 62 ድምጽ ነበር ያገኘነው፡፡
ምን አይነት ንግግር ቢያደርጉ ነው መራጮችን መማረክ የቻሉት?
እኔ የተናገርኩት ብዙ ከባድ ንግግር አይደለም፡፡ ምን አልኩ መሰለሽ? “እኔ እንደ ድሮ ፓርላማ - መንገድ አሠራላችኋለሁ፣መብራት አስገባላችኋለሁ አልልም፡፡ ከአዲስ አበባም ልመረጥ ከሌላም ልወከል ለላከኝ ክልል ወይም ቻምበር ሳይሆን ለሁላችሁም የኢትዮጵያ ማህበር አባላት በቀናነት አገለግላለሁ፡፡ ነገር ግን ከዚህ ከተወከለች ለእኛ ትሠራለች ለዚህኛው ወገን በቅርበት ትሠራለች የሚል የተከፋፈለ ሃሳብ ካላችሁ አትምረጡኝ፡፡ ለእውነትና ለሃቅ ፊት ለፊት የምጋፈጥ ስለመሆኔ ታውቃላችሁ” ከዚህ በላይ ብዙ መናገር አላስፈለገኝም ነበር፡፡
የሃላፊነት ቦታው ግን እስካሁን ድረስ ከሽኩቻ እንዳልፀዳ ይነገራል------
በፊት የነበሩ ሰዎች መቀጠል ነበረብን የሚል ቁጭት አለ፣ አሁንም የሷን ስራ እናበላሻለን ይላሉ፣ የኔ ሳይሆን የመንግስትና የህዝብ ስራ ነው የሚሠራው፡፡ ስለዚህ ይሄ ነገራቸው የበለጠ እንድንሰራ ያደርገኛል እንጂ አያሰንፈኝም፡፡
የድሮ ሰው ምቀኛ አታሳጣኝ የሚለው ለምን ይመስልሻል፡፡ ሰው ሲቃወምሽ አንዳንዴ ስህተትሽንም ትመለከቻለሽ፣በጭፍን ጥላቻ የሚያወራብሽም ከሆነ ዘግተሽው ስራሽን ትቀጥያለሽ አለቀ፡፡ በወሬ ጊዜያቸውን ባያባክኑ ግን ደስ ይለኛል፡፡ እኛ በአሉባልታ ጊዜ እንድናባክን ይፈልጋሉ፣እኛ ለወሬ ጊዜ የለንም አለቀ፡፡ ሥራ ላይ ነን፡፡ ለውጥ ላይ ነን፡፡
አሸንፈው ሃላፊነቱን ሲረከቡ በቅድምያ የጠበቅዎት ስራ ምን ነበር? እስካሁንስ ምን አከናወኑ?
ብዙ ሊስተካከሉ የሚገቡ ሥራዎች ሊጠብቁሽ ይችላሉ፡፡ አንድ አገርኛ አባባል ልንገርሽ፡፡ የዱሮ ባሎች የመጀመርያ ሚስት ፈትተው ሌላ ሚስት ሲያገቡ፣ አዲስ የተገባችው ሴት የመጀመሪያዋ የሠራችውን መደብ አፍርሳ ከዛ የባሰ የተበላሸ መደብ ትሠራለች ይባላል፡፡ እሷ ያንን የምታደርገው ከጀመሪያዋ የተሻልኩ ነኝ ለማለት ነው፡፡ እኔ እንደ አዲሷ ሚስት ያለ አመለካከት የለኝም፡፡ አዲስ የተመረጡት የቦርድ አባላትም ጭምር፡፡ እከሌ በነበረበት ጊዜ ይህን አላደረገም ይህን አበላሽቷል ብሎ የማጣጣል ፍላጐትም ሃሳቡም የለንም፡፡ በነበረው አሠራር ጥሩ ነው ያለውን እንቀጥልበታለን፡፡
የተበላሹ ካሉ እያስተካከልን የመሄድ ሃሳብ ነው የነበረን፡፡ በጣም የሚገርምሽ የምርጫው ዕለት እኔ ሳሸንፍ ህዝቡ “ሳዳም ወረደ፤ጋዳፊ ወረደ” እያሉ ሲጨፍሩ ሊቀመንበሩ ማስቆም አልቻሉም ነበር፡፡ እኔ ድምጽ ማጉያውን ተቀብዬ “ከእኔ ጋር መስራት የምትፈልጉ ከሆነ እንዲህ አይነት ንግግር አልፈልግም፡፡ እኔ የሠላም አምባሳደር ነኝ፤ በሠላምና በፍቅር ነው መስራት የምፈልገው፡፡ የሚሠራው ሰው ይሳሳታል ያጠፋል፤ ያም ቢሆን እስከዛሬ ያገለገለ ሰው መመስገን እንጂ መሰደብ የለበትም፤አሁኑኑ ይህን አይነት ስድብና ጭፈራ ካላቆማችሁ ትቼ እሄዳለሁ” ስል ሁሉም በአንድ ጊዜ ፀጥ አሉ፡፡
ይታይሽ “ሳዳም ጋዳፊ ወረደ” የሚሉት እሳቸው ባሉበት ነው፤ የሠራ ሰው በፍፁም መሰደብ የለበትም፡፡ በእለቱ እኔ ምን አልኩኝ፤“ድግስ ደግሰን ጋብዘን ሸልመንና አመስግነን እንሸኛቸዋለን” ይህንንም አድርገናል፤ሚኒስትሮች ባሉበት ራት ጋብዘን፤ ለቦርዶቹ ደረት ላይ የሚደረግ የቻምበሩ አርማ ያለበት ወርቅ ሸልመን ነው የሸኘናቸው፡፡
ሥራውን ሲጀምሩት በጣም ፈታኝ የሆነብዎ ምን ነበር?
በጣም ፈታኝ የምለው ስራ በኢትዮጵያና በአዲስ አበባው ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤቶች መካከል ጠብ ነበር፡፡ ጠላትነታቸው ደግሞ ለ40 ዓመታት ሥር የሰደደ ነው፡፡ እኔ ወደ ኢትዮጵያ የንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ስመጣ ሁኔታው በጣም የከፋ ነበር፡፡ ብቻ ምናለፋሽ ጥሩ ሁኔታ አልነበረም፡፡ ሰዎች የሁለቱን ቻምበሮች ጉዳይ እንዳትነኪ፤ ዝም ብለሽ ቀጥይ ይሉኝ ነበር፡፡
የጠባቸው መንስኤ ምንድን ነው?
አንዱ የሚያጣላቸው የህንፃው ጉዳይ ነው፡፡ ሌላው የስራ መመሳሰል ነው፡፡ ለምሣሌ አዲስ አበባ ቻምበር ይህን ይሠራል፤የኢትዮጵያ ይህን ይሠራል እየተባባሉ፡፡ ተባብረውና ተቻችለው መስራት ሲችሉ ይበጣበጡ ነበር፡፡ እኔ ለጉዳዩ እልባት ለማግኘት ስሞክር፤ሁለቱን ቻምበሮች ለማስታረቅ እንዳትሞክሪ፤የህንፃውን ጉዳይ እንዳትነኪ እባላለሁ፡፡ እኔ ደግሞ መስራት ካለብኝ ሠላምና የረጋ መንፈስ ባለው ሁኔታ ነው የምሠራው፡፡ ይህን አትንኪ ያንን አታንሺ የሚባለውን ነገር አላመንኩበትም፤እስከመቼ ነው ሳትነኪ የምትኖሪው? ችግርን ቀርበሽና ተጋፍጠሽ እንጂ በመፍራትና በመሸሽ መፍትሔ አታመጪለትም፡፡
ከቦርድ አባላት ጋር ተነጋግሬ ይህን ጭቅጭቅና ጠብ ፈትተን በሠላማዊ መንገድ መስራት አለብን በሚል ብዙ ሥራዎች ተሠሩ፡፡ መጀመሪያ ኮሚቴ አቋቋምኩኝ፤የሚጣሉበትን ነገር አጣራን፤ኮሚቴው የውሳኔ ሃሳብ ሲያቀርብ የሚበጣበጡ ሰዎችን ኮሚቴ ውስጥ በመክተት ገለልተኛ የሆኑ ሰዎችንም ጨምሬ በሠላማዊ መንገድ ተነጋግረን ችግሩን ፈታን፡፡ አንድ ወር ተኩል ባልሞላ ጊዜ ነው ችግሩ የተፈታው፡፡
የህንፃውን ጉዳይ በተመለከተ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር በደብዳቤ ባሳወቁት መሠረት፤ “አዲስ አበባ ቻምበር በባለቤትነት ይዞት አዲስ አበባም ሆነ ሌሎች የክልል ቻምበሮች እንዲገለገሉበት፤የራሳቸውን ህንፃ እያሰሩ ሲወጡ ቀሪው ለኢትዮጵያ ቻምበር እንዲሆንና እያከራየ እንዲጠቀም እንዲሁም የክልል ቻምበሮችን እንዲያጠናክርበት ይሁን” በሚል ተስማምተን አሁን በፍቅርና በሠላም ብዙ ነገሮችን በጋራ እንሠራለን፡፡ አሁን እንደውም እኛ ስራ ሲበዛበን አዲስ አበባ ቻምበሮችን አግዙን እንላለን፤ እኛም እነሱን እናግዛለን፡፡ እንደ ዱሮው መገለማመጥና የጐሪጥ መተያየት ፈጽሞ ተወግዷል፡፡ በአመት ሁለት ጊዜ የመገናኛና የመሰብሰቢያ ፕሮግራም ሁሉ አዘጋጅተው እርስ በእርስ ይገባበዛሉ ይጨዋወታሉ፡፡
ከመንግስት ቢሮዎችና ከንግዱ ጋር ከተገናኙ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች ጋር ያላችሁ የስራ ግንኙነት ምን ይመስላል?
ከ10 እና ከ15 ዓመት በፊት ሲለፋበት የኖረን ጉዳይ ነው፤ አሁን እኛ በተሳካ ሁኔታ እየሠራን ያለነው፡፡ ለምሣሌ ከንግድ ሚኒስቴር፣ከኢንዱስትሪ ሚኒስቴር፣ከገቢዎችና ጉምሩክ፣ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ከጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ ወዘተ ስንተዋወቅና አብረን መስራት እንፈልጋለን ስንል ሁሉም እውነት አልመሰላቸውም ነበር፡፡ ምክንያቱም ንግድ ምክር ቤት ከመንግስት ጋር አብሮ መስራት አይፈልግም የሚል እምነት ነበራቸው፡፡ እኛ ግን ከመንግስት ጋር የመስራት ጽኑ ፍላጐት አለን፡፡ ምክንያቱም ህግና ፖሊሲ የማያወጣው መንግስት ነው፡፡ ህግና ፖሊሲ ከሚያወጣ መንግስት ጋር አብሮ አለመስራት ደግሞ መልካም አይደለም በሚል ተነጋግረን፣ ከእነርሱ ጋር ሁለትና ሶስት የምክክር መድረኮች አካሂደናል፡፡ ይህን በብሔራዊም በክልልም ደረጃ አድርገነዋል፡፡ ከተመካከርንባቸው ውስጥ የወደብ ዕቃ ማንሳት ጉዳይ፣ ህዝቡ የተጯጯኸበት የንግድ ምዝገባ ጉዳይ፣ የታክስ አከፋፈልና የመሳሰሉት ላይ ተወያይተን አሁን ህጉን ሊያሻሽሉት ነው፡፡ ለምሣሌ ከጉምሩክ ጋር ባካሄድነው ውይይት ከመንግስት ጋር ይጣላሉ ተቀባይነት አያገኙም ሲሉን፣ መንግስት 98 በመቶውን የኛን ሃሳብ ተቀብሏል፡፡ ከላይ በጠቀስኩልሽ በታክስ አከፋፈል፣ በወደብ ዕቃ አነሳስ፣ በንግድ ምዝገባና በበርካታ ጉዳዮች ለንግዱ ማህበረሰብም ሆነ ለመንግስት ይጠቅማሉ ባልናቸው ሃሳቦች ላይ ነው መንግስት 98 በመቶ ሃሳባችንን የተቀበለው፡፡ “ያልተጠበቀ የመንግስት አቋም” ተብሎ ተወድሷል፡፡ በአጠቃላይ ያተኮርነው ለንግዱ ህብረተሰብ ምቹ የንግድ ከባቢን የመፍጠር ስራ ላይ ነው፡፡
አገሪቱ ውስጥ የተለያየ ፍላጐትና ባህሪ ያላቸው ነጋዴዎች አሉ፡፡ የንግዱን ማህበረሰብ የማስተዳደሩ ጉዳይ ምን ይመስላል?
እኛ የአገሪቱ የንግድ ማህበረሰብ ጥሩ ስነ - ምግባር ያለውና ታማኝ እንዲሆን የማንቃት፣ በተሳሳተ መንገድ የሚጓዙ ካሉ ወደ መስመር የመመለስ፣በሰዓቱ ግብር እንዲከፍሉና በንግድ ሥራ የሀገራቸውን መልካም ገጽታ እንዲገነቡ ጥረት እያደረግን ነው፡፡ እርግጥ ነው በርካታ ነጋዴዎች አሉ፣የተለያየ ባህሪ መኖሩም አይካድም፣ ነገር ግን በመልካም አቀራረብና አዎንታዊ መንፈስ በተሞላበት ሁኔታ ችግሮቻችንን እንፈታለን፡፡
የነጋዴውን ጥቅም በማስከበርና ከመንግስት ጋር ቅርርብ እንዲኖር የበኩላችንን እያደረግን ነው፡፡
አባላቱ በርካታ ቢሆኑም ነጋዴውን በመቅረብና በማነጋገር በቀላሉ ጤናማ በሆነ መንገድ መምራት ይችላል፡፡
በደርግ መንግስት ተወርሶ የነበረው ህንፃችሁ ተመልሶላችኋል፡፡ ሆኖም አዲስ ህንፃ ለማስገንባት ለአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ የቦታ ጥያቄ ማቅረባችሁን፣ምን ያህል ቦታና የት ቦታ እንደምትፈልጉ ከንቲባ ኩማ ደመቅሳ አሳውቁን ማለታቸውን ሰምቻለሁ፡፡ ያሁኑ ህንፃ እያለ ሌላ መገንባት የፈለጋችሁት ለምንድን ነው? ህንፃውን የምትገነቡበት ገንዘብ ከየት የሚገኝ ነው? ምን አይነት ህንፃስ ለማስገንባት አሠባችሁ?
ህንፃውን የማስመለስ ሥራ ረጅም ጊዜ ወስዷል፡፡ ከአስራ አምስትና አስራ ስድስት ዓመት በላይ ማለት ነው፡፡ ይሄ ህንፃ የተሠራው የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ሳይመሠረት በፊት ነው፤ አዲስ አበባ ንግድ ምክር ቤት በሚል የተሠራው፡፡ ስለዚህ አዲስ አበባ ቻምበር ይመለስልኝ ይላል፡፡ ኢትዮጵያ ቻምበርም ይመለስልኝ የሚል ደብዳቤ ሲያስገባ ቆይቷል፡፡ በኋላ ግን እኛ ምን አልን ---- የሚመለስ ከሆነ ለኢትዮጵያም ሆነ ለአዲስ አበባ ይመለስ የሚል አቋም ላይ ደረስን፡፡ በዚህ ሁኔታ መንግስት ህንፃውን ሲመልስ ኢትዮጵያ ቻምበር በባለቤትነት ይያዘውና መጠቀሙን አብረው ይጠቀሙ ሲል፤ አዲስ አበባ ደግሞ ኢትዮጵያ ቻምበር ሳይፈጠር የራሴ ነበር ይላል፡፡ ይሄው ይጠቀሙ ሲል አዲስ አበባ ደግሞ ኢትዮጵያ ቻምበር ሳይፈጠር የራሴ ነበር ይላል፡፡ ይሄ ጭቅጭቅ በነበረበት ወቅት እኛ በጭቅጭቅ ጊዜም ገንዘብም ከምናባክን ለአንዳችን ተመልሶ በጋራ ለምን አንጠቀምም፤ ከዚያስ ለምን የራሳችንን ህንፃ አንሰራም በሚል የአዲስ አበባው ንግድ ምክር ቤት ቦታ ጠይቆ ስራ ጀምሯል፡፡
እኛም ቦታ የጠየቅነው ለዚህ ነው፡፡ ህንፃው ከሁለት ዓመት በፊት ከተመለሰ በኋላ ግን ተከፋፍሎ በሠላም መጠቀም አልተቻለም፡፡ ስለዚህ እኛ ተመካክረን መንግስትን የወሰነውን ተግባራዊ ወደማድረግ ሄድን፡፡
ምክንያቱም መንግስት በዚህ በዚህ መልኩ ይጠቀሙ የሚል መመሪያ አስቀምጧል፡፡
አዲሱን ህንፃ ለመገንባት የታሰበበት ዋናው ምክንያት በየሀገሩ ሄደን የንግድ ምክር ቤት ቢሮዎችን ስንጐበኝ የምናያቸው ከእኛ ጋር ፈጽሞ አይገናኙም፡፡ የእኛ በጣም ያሳፍራል፡፡ የውጭዎቹ የአብዛኛዎቹ ቢሯቸው ህንፃው ራሱ ቤተ - መንግስት ነው የሚመስለው፤የእኛ ግን ከ60 እና 70 ዓመት በፊት የተሠራ ህንፃ ነው፡፡ እንደውም ያኔ ባለራዕይ ሆነው ይሄን ሰሩ እንጂ አሁን ያለበት ሁኔታ እንኳን ከአለም አቀፍ ንግድ ምክር ቤቶች ከክልል ምክር ቤቶች ጋርም መወዳደር አይችልም፡፡ በዚህ ምክንያት የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባን ቦታ ጠይቀናል፡፡ አለምአቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የስብሰባ አዳራሽ፣ ቢሮዎች በአጠቃላይ የትኛውም አለምአቀፍ ሰው ቢመጣ አንገታችንን ቀና አድርገን የምናስገባበት መሆን መቻል አለበት፡፡ አሁን የአገራችን ኢኮኖሚ እያደገ ስለሆነ ብዙ ባለሀብቶች ኢትዮጵያ ውስጥ ኢንቨስት ለማድረግ እየመጡ ነው፡፡ ሲመጡ ደግሞ ንግድ ምክር ቤቱን ያነጋግራሉ፡፡ ያኔ የእኛ ቢሮ እንዲህ የሚያሳፍር ከሆነ ልክ አይመጣም፤ስለዚህ ቦታውን ሊሰጡን ፈቃደኛ ናቸው፡፡ ሁሉም ክልሎች ቦታ ተሰጥቷቸው ንግድ ምክር ቤት እንዲሠሩ እያልን ነው፡፡ የድሬዳዋው ንግድ ምክር ቤት ህንፃ እንዲመለስ ደብዳቤ መንግስት ጽፏል፤አፈፃፀም ነው የቀረው፡፡ በሌላ በኩል የንግዱ ማህበረሰብ ድምጽ እንዲሰማና ትኩረት እንዲያገኝ የአባላት ማብዛት ሥራ በከፍተኛ ሁኔታ ተሠርቷል፡፡ ለምሳሌ ትግራይ 16ሺህ ደርሷል፡፡ ደቡብም አማራም የአባላት ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ አድጓል፡፡ ጠንካራ ስራ ሠርቶ አባላትን በከፍተኛ ሁኔታ ላበዛ ክልል ሽልማት እንሸልማለን ብለን ሁሉም በፉክክር በጥሩ ሁኔታ እየሠራ ነው፡፡ አሁን የምንጠይቀው መሬት በከተማ ውስጥ ሆኖ ስፋቱም ምክንያታዊ የሆነ ነው፡፡
መጀመሪያ ለቢሮ ነው የምንጠይቀው፡፡ ከዚያ በኋላ አለም ዓቀፍ ኤግዚቢሽን የምናሳይበት ከከተማ ውጭ ቦታ መጠየቃችን አይቀርም፡፡
ቻምበር አካዳሚ ለማቋቋም ሀሳብ እንዳላችሁ ሰምቻለሁ፡፡ ምንድነው የሚሰራው? ዘርዘር ያለ ማብራሪያ ቢሰጡኝ----
ቻምበር አካዳሚ የሚለውን ስም አስጠንተናል ቻምበር አካዳሚ ከሚባል በቀላሉ “ሊደርሺፕ ኢንተርፕሪነርሺፕ ኤንድ ማኔጅመንት ሴንተር” እንዲባል ተስማምተናል፡፡ አመራርን፣ ስራ ፈጠራን እንደዚሁም ሥራ አመራርን አካትቶ ከተቋቋመ የላቁ ሰዎችን - መሪዎችን፣ የቦርድ አመራሮችን፣ የአገር መሪዎችን ወዘተ ከአፍሪካም ሆነ ከዓለም የሚያሰለጥን የልቀት ማዕከል ሊሆን ይችላል፡፡ ሥራ ፈጠራ ላይ በተለይ የሚያሰለጥን በቂ ተቋም የለም፡፡ ስለዚህ ሰዎች ችግር ከመፍራት ይልቅ መፍትሔ ፈጣሪ እንዲሆኑና የአስተሳሰብ ለውጥ እንዲያዳብሩ ማስተማር የሚችል ማዕከል ይሆናል፡፡ በማኔጅመንትም በኩል አገራችን ላይ ጉልህ የማኔጅመንት ችግር አለ፡፡ ስለዚህ ሰዎች በብቃት የመምራትና የማስተባበር ችግርን አስወግደው የላቀ ብቃት የሚያገኙበት ይሆናል፡፡ ይህንን ስንልም ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለዓለምም ነው፡፡ ለምሣሌ ኢትዮጵያ አየር መንገድ ከውጭ ሁሉ መጥተው የሚሠለጥኑበት ሆኗል፡፡ ራዕይ ባላቸው ሰዎች ነው አየር መንገዱ ለዚህ የደረሰው፡፡ አሁን የእኛን ሃሳብ የሚያጣጥሉ አንዳንድ ሰዎች አሉ፤ ነገር ግን በእርግጠኝነት ዕውን እናደርገዋለን ብለን እናስባለን፡፡
በአሁን ሰዓት የመጀመሪያዋ ሴት የኢትዮጵያ የንግድ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ለመሆን በቅተዋል፤ የመጀመሪያዋ ሴት ጠቅላይ ሚኒስትር የመሆን ሃሳብስ የለዎትም?
(ሣ…ቅ) እኔ ፖለቲከኛ አይደለሁም፡፡ ፖለቲከኞች ናቸው ለስልጣን ተነሳስተው የሚሄዱት፡፡ እኔ እዛ ወጥቼ ባልመራም በየትኛውም ቦታ ላይ መሪ ነኝ ብዬ አምናለሁ፡፡ ለምሣሌ እኔ ጥሩ ሃሳብ አምጥቼ የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሥራ ላይ ካዋለው እኔ ነኝ የመራሁት ማለት ነው፡፡ ለምሣሌ አንቺ ለጠቅላይ ሚኒስትር ኀይለማርያም ጥሩ ሃሳብ አቅርበሽ ሥራ ላይ ካዋሉት የመራሽው አንቺ ነሽ፡፡ ብዙ ጊዜ ሰዎች የሚያዩት ወንበር ላይ መቀመጡን ነው፤ እኔ ግን የምፈልገው ስራ መሠራቱን ነው፡፡ አንቺ ከልብሽ ከሠራሽና ከተንቀሳቀሽ አንቺ ባትፈልጊም ስራው ይፈልግሻል፡፡
የጠቅላይ ሚኒስትርነቱ ጥያቄ ገፍቶ ቢመጣስ አልፈልግም ትያለሽ?
አዎ እምቢ እላቸዋለሁ፡፡ ለምን መሠለሽ? እናንተ ምሩ፤ እኛ ከኋላ እናሠራለን እላቸዋለሁ፡፡ እኔ ፖለቲከኛ ስላልሆንኩ ነው፡፡ እዛ ቦታ ላይ መቀመጥ ያለባቸው ፖለቲከኞች ናቸው፡፡ አንድ ጋዜጠኛ ባለፈው ለምንድነው ፖለቲካ ውስጥ የማትሳተፊው ሲለኝ ነበር፡፡ እኔ ግን የፖለቲካውን ቼዝና ዳማ ጨዋታ አልችልበትም፡፡ እኔ ፊት ለፊት የምናገር ሰው በመሆኔ የፖለቲካውን ድራማ አልችልም ብዬ መልሼለታለሁ፡፡
ይሄ የብቃት ጉዳይ አይደለም፤ሞክሮ መውደቅም ይቻላል፡፡ ለአንድ ሰው ዋናው ነገር የተቀመጠበት ቦታ ሳይሆን በቀናነት ባለበት ቦታ መስራት መቻሉ ነው፡፡ ቀና ሰው ስለሆንሽ ችግር አይገጥምሽም ማለት አይደለም፡፡ ብዙ ችግርና እንቅፋት አለ፡፡ ያንን እንቅፋት ረግጠሽ አንቺ ወደ ላይ ከፍ ማለት ነው ያለብሽ፡፡
አንዳንዱ የአንዱን ትከሻ ረግጦ ራሱ ከፍ ማለት ይፈልጋል፡፡ እኛ እንኳን ባለንበት ቦታ ብዙ ጫና አለ፡፡
እኔ አሁን ስራውን የቀጠልኩት ለችግርና ለመከራ ስለማልበገር ነው፡፡ እንቅፋት እኮ ከኖርማሉ መሬት ከፍ ያለ ነው፤ስለዚህ እዛ እንቅፋት ላይ ስትቆሚ የባሰ ከፍ ትያለሽ፡፡ ለዚህም ነው እኔ ከመከራ በላይ ነኝ ብዬ የማምነው፡፡
የቤተሰብ ሃላፊነት አለ፣ የስራ ሃላፊነት አለ፣ አሁን ደግሞ ለፒኤችዲ እየተማርሽ ነው፡፡ ይህን ሁሉ ሃላፊነት በአንድ ላይ መወጣት አይከብድም? እንዴት እየተወጣሽው ነው?
ይሄ የጊዜ ጉዳይ ነው እንግዲህ፡፡ አንዳንዴ በቻምበሩ በኩል በሙያሽ ከምትሠሪው በተጨማሪ በርካታ ስራዎች ይመጣሉ፡፡ ሌላው ቀርቶ ዛሬ ነፃ ነኝ ብለሽ ስታስቢ ያላሰብሻቸው ሥራዎች በፀሐፊዋ በኩል ይቀርቡልሻል፡፡
አለም አቀፍ ስብሰባ መምራት፣ የተለያዩ ሪሴፕሽኖች ላይ መገኘት የመሳሰሉት ለምሣሌ በአንድ ምሽት ሶስት ሪሴፕሽን ላይ እንድትገኚ ይፈለጋል፡፡ እኔ አንዱ ጋ ሄጄ ሌላው ጋ አንድ የቦርድ አባል ስልክ፣ ለምን ፕሬዚዳንቷ አልመጣችም ይላሉ፡፡ ስለዚህ አንዱ ጋ ቶሎ ግንባሬን አስመትቼ ሌላው ጋ ደግሞ እሮጣለሁ፡፡ ቻሌንጁ ብዙ ነው ግን ቁርጠኛ ከሆንሽ የማይሰራ የለም፡፡
ብዙ ጊዜ በዕቅድ እንቀሳቀሳለሁ፣ነገር ግን እቅዴን የሚያበላሹ ነገሮች ይመጣሉ፣አቻችሎ መሄድ ነው፡፡ እቤት ውስጥ እኔ ከሌለሁ የቤት ሠራተኛ አበላሽታ የምትጠብቅሽ ነገር ይኖራል፣የቤቴን መበላሸት ግን ከአገር ጉዳይ አላስቀድምም፤ ወደ መንግስት ሥራ እሄዳለሁ፤የትምህርቱም ጉዳይ በዚህ መልኩ ነው የሚሄደው፡፡ እኔ በትምህርት ልምዱ ስላለኝ ክላስ ሳልከታተል የምሠራቸው ስራዎች አሉ፡፡
ቃለምልልሱን ከማጠናቀቃችን በፊት ስኬት ለእርስዎ ምን ማለት እንደሆነ ቢነግሩኝ----
ስኬት ማለት ሰው የፈለገውን መሆን መቻል ነው፡፡ አንድ ሰው ስኬት ብሎ የሚያስበው በ10 ደቂቃ 100 ሜትር መሮጥ ሆኖ በሳምንትም ሆነ በ10 ደቂቃ ከጨረሰ ስኬት ነው፤ ግን ያ የስኬቱ መጨረሻ ሊሆን አይገባም፡፡ ከዛ የተሻለ ስራ ለመስራት መነሳት አለበት፡፡ አንድ ሰው ግቡ ጋ ሲደርስ ስኬት ነው፡፡
ግን የስኬቱ መጨረሻ መሆን የለበትም ብዬ ነው የማምነው፡፡
እኔ ሁሌም ችግርን መከራን አሸንፋለሁ፡፡ ለሌላ ስኬት እዘጋጃለሁ፡፡ በአጠቃላይ ለእኔ ስኬት ቀጣይነት ያለውና መሆን የምትፈልጊውን መሆን ማለት ነው፡፡

በኢትዮጵያ በ1920ዎቹ የነበረው ታሪክ ዛሬ ሲያስቡት ተረት ይመስላል፡፡ የኢትዮጵያ የጦር-ባላባቶች፤ ሰው ኃይለሥላሴ የሚባል (ራስ ተፈሪም የሚባል ስም አለው) አንድ ወጣት በአሰርታት ዓመታት ውስጥ መሪ ሊሆን ማኮብኮቡን ሰሙ፡፡ ይሄ ጭምት መሳይ ዝምተኛ ሰው አገሪቱን የመቆጣጠር አቅም እንደሚኖረው ሊገባቸው አልቻለም፡፡ ሆኖም በ1927 ዓ.ም ኃ/ሥላሴ እያንዳንዱ በየተራ እንዲመጣና ታማኝነታቸውን በመግለፅ መሪያቸው መሆኑን እንዲያረጋግጡ አዘዘ፡፡
አንዳንዶች በጥድፊያ፣ አንዳንዶች ፈራ-ተባ እያሉ ትእዛዝ ሲፈፅሙ፤ የሲዳሞው ደጃዝማች ባልቻ ግን አሻፈረኝ አለ፡፡ ኃይለሥላሴ በተለመደው የጨዋና ግትር ዘዴው፤ ባልቻ እንዲመጣ ተማፀነው፡፡ ባልቻም “እታዘዛለሁ ግን በፈለኩት ጊዜ ነው የምመጣው፡፡ በተጨማሪም 10,000 ጦር ይዤ ነው ከአዲስ አበባ ወጣ ብዬ እምጠብቀው” አለ፡፡
ኃ/ሥላሴም፤ “ስለክብርህ የፌሽታ ግብዣ ላደርግልህ አስቤአለሁና፤ ተጋበዝልኝ” አለ፡፡ ባልቻ ግን ታሪክን ጠንቅቆ ያውቃልና የቀደሙት የኢትዮጵያ ነገሥታትና መሳፍንት ግብዣን እንደወጥመድ ሲጠቀሙበት እንደኖሩ ተገንዝቧል፡፡ ነቄ ነው፡፡ መታሰርም ሆነ መገደል የሚከተለው ከግብዣ በኋላ ነው፡፡
ደጃዝማች ባልቻ የግብዣውን ዓላማ እንደተረዳ ለመጠቆም “የምመጣው 600 ክብር ዘበኞቼን ይዤ ነው” አለ፡፡ ኃ/ሥላሴ ግን “እንዲህ ያሉትን ጀግኖችህንማ ማስተናገድ ለእኔ ክብር ነው” ሲል መለሰ፡፡
ባልቻ ክቡር ዘቦቹን ግብዣው ላይ እንዳይሰክሩና በተጠንቀቅ እንዲጠብቁ አዘዘ፡፡ ግብዣው ቦታ ሲደርሱ ኃ/ሥላሴ ታይቶ የማይታወቅ አቀባበል አደገ፡፡ ባልቻ “ማምሻውን ወደ ጦር ሰፈሩ መመለስ አለብኝ፤ አለበለዚያ ጦሬ አዲስ አበባን እንዲወርር አዝዣለሁ” አለ፡፡ ኃ/ሥላሴ ባለመታመኑ እንዳዘነ በመግለፅ፤ ይልቁንም ከግብሩ በኋላ የሚዘፈነው ዘፈን የሲዳሞን ጦረኛነት የሚያረጋግጥ እንዲሆን አደረገ፡፡ ባልቻም ኃ/ሥላሴ የፈራና ለማይረታው ወታደሩ እጁን የሰጠው መሰለው፡፡
ከሰዓት በኋላው ሲገባደድ ባልቻና ወታደሮቹ ነጋሪት እያስጐሰሙ ወደ ጦር ሠፈራቸው አመሩ፡፡ ከሳምንታት በኋላ አዲስ አበባን መውረር እንደሚችል አሰበና ባልቻ ኃ/ሥላሴ እንግዲህ ቦታው ወይ ዘብጥያ ወይ ሞት ነው” አለ፡፡
ሆኖም ባልቻ ወደ ጦር ሠፈሩ አካባቢ ሲደርስ አንድ የተሳሳተ ነገር መኖሩን ተገነዘበ፡፡ አንድም ድንኳን የለም፡፡ የሚታየው ጭስ ብቻ ነው፡፡ አንድ የዐይን ምስክር የሆነውን ሁሉ አስረዳው፡- የኃ/ሥላሴ ጦር ባሳቻ መንገድ መጣ፡፡
የመጣው ግን ሊዋጋ አልነበረም፡፡ ኃ/ሥላሴ በዘምቢል ወርቅና ብር አጭቆ የላከው ጦር ነው፡፡ የባልቻን ወታደሮች መሣሪያ ሁሉ በወርቅና በብር ገዛ፡፡ እምቢ ያሉ ተያዙ፡፡ በጥቂት ሰዓት ውስጥ የባልቻ ጦር መሣሪያውን አስረከበ፡፡ ባልቻ ወደ ደቡብ 600 ወታደር ይዞ ለመሸሽ ቢፈልግም ያ መሣሪያ የወሰደባቸው የኃ/ሥላሴ ወታደር መንገዱን ገትሮ ይዟል፡፡
ወደ አዲስ አበባ እንዳያቀና ሌላ ጦር መንገዱን ገድቦታል፡፡ እንደቼዝ ተጨዋች ዙሪያውን ተከበበ፡፡ ባልቻ ለመጀመሪያ ጊዜ እጁን ሰጠ፡፡ በኩራትና በአጉል ምኞት የሠራው ኃጢያት ስለፀፀተው ወደ ገዳም ሊገባ ተስማማ፡፡ ያለ አንዳች የጥይት ድምፅ ኃ/ሥላሴ ደጃዝማች ባልቻን አስወገደ፡፡
የሲዳሞው ደጃ/ባልቻም ወደ ገዳሙ ከመግባቱ በፊት፤
“የተፈሪን ጉልበት አትናቁ፡፡ እንደ አይጥ ይድሃል፡፡ ሆኖም የአንበሳ ጥርስ ነው ያለው!” አለ፡፡
***
በግብዣ ከመጠመድ ይሰውረን! የሌሎችን ጉልበት ከመናቅ አባዜ ያድነን፡፡ የራስን አቅም የዓለም መጨረሻ ነው ብሎ ከማጋነን ይሰውረን! የመስተዋት መስኮቱን ጭሳማ የማድረግ ጥበብ ያለው አለቃ ወይም የፖለቲካ መሪ፤ ጭሳማውን ቀለም የበለጠ ባጠቆረው መጠን፣ የበለጠ እንዳናየው እያደረገ መሆኑን አንርሳ፡፡ “ጦርነቱን ከማወጅህ በፊት ድልን ተቀዳጅ” ይላሉ ፈረንጆች፡፡ እቅድህን አታሳውቅ፡፡ ስለእቅድህ ከመፎከር ተጠንቀቅ ነው ነገሩ፡፡ ባላንጣህ እቅድህን እንዳያውቅ ባደረግህ ቁጥር የድልህ መጠን ይበልጥ እየሰፋ ይመጣል፡፡ ስለእቅድህ በፎከርክ ቁጥር ግን ስኬትህን እያራቅህ ነው የምትሄደው፡፡ የሞቀ ከተማ እያሰብን መጨረሻችን ገዳም የሚሆነው ሥር-ባልሰደደ ድል ስንኩራራና ሌሎች ስለእኔ ምን ያስባሉ ብለን ሳንጠይቅ ስንቀር ነው፡፡
በቡድናዊ ስሜት አለመጠመድና አለመጨፈን ለአገርና ለህዝብ የሚበጅ አካሄድ ነው፡፡ ምክንያቱም አስተሳሰባችንን እያጠበብን የቡድናዊ ስሜት ተገዢ ስንሆን ደባንና ሴራን የሙጥኝ ወደማለት እንገባለን፡፡ ያ ደግሞ አደገኛ ነው፡፡
የሦስተኛው ክፍለ - ዘመን ህንዳዊ ፈላስፋ - ካውቲላ፤
“በዓላሚ ቀስተኛ፣ የተሰደደ ቀስት
አለው አጋጣሚ፣ ወይ ሊገል ወይ ሊስት፡፡
ግን በስል-ጭንቅላት፣ ሤራ ከተሳለ
ህፃንም ይገድላል፣ እናት ሆድ ውስጥ ያለ፡፡”
የሚለን ለዚህ ነው፡፡
ሌላው የአገር ጉዳይ ግልብ - እውቀትን መከላከል ነው - ባልበሰለ አዕምሮ ዘራፍ ማለትን፡፡ ያለፖለቲካዊ ብስለት ፖለቲከኛ ነኝ ማለትን፡፡ መላው ዓለም እውቀት ሆኖ ሳለ የአዕምሮን በር ዘግቶ፣ የእኔ እውቀት ብቻ ነው ገዢ ብሎ ማሰብ ክፉ አባዜ ነው፡፡ ከሳጥኑ ውጪ (Out of the box እንዲሉ) ለማየትና ለማስተዋል አለመቻል፤ የሌሎችን ሀሳብ ለመቀበል ዝግጁ አለመሆንን ያስከትላል፡፡ ያ ደግሞ ብዙ አለመግባባቶችን ይወልዳል፡፡ “ከመርገምት ሁሉ የከፋው መርገምት ቋንቋ ለቋንቋ መጠፋፋት” ይለዋል ባለቅኔው፡፡ ወጣቱ፤ መሰረታዊ እውቀት፣ ጥልቀትና ብስለት፣ ከዚያም ስክነትና ጥበበኛነት እንዲኖረው ለማድረግ ብርቱ ጥረት ያስፈልጋል፡፡ አዋቂው ራሱን እንዳያጥርና እንዳይገድብ፣ ልምዱን እንዲያጋራ መንገድ መክፈት ያሻል፡፡
ለሁሉ የህይወት ዘርፍ ፖለቲካዊ ትርጉምና አንድምታ ሰጥተን አንችለውም፡፡ መሰረታዊ እውቀት፣ ከኑሮ የምንቀስመው ልምድና ከባህል ያበለፀግነው የአእምሮ ሀብት የህይወትን ትርጉም ለማየት በዋናነት መሣሪያዎቻችን ናቸው፡፡ ይህንንም ለመቀበል እውነተኛ የህዝብ ፍቅር ያስፈልጋል፡፡ እውነተኛ የህዝብ ፍቅር የራስን ጥቅም መሰዋትን ይጠይቃል፡፡
“ህዝብን በመጠቀም የራስን ግብ ለመምታት ያለው ዘዴ በጉልበትና በማጭበርበር የሚደረግ ነው፡፡ ይልቁንም የህዝብ ፍቅር አንዱ መሣሪያ ነው ይላሉ ጠበብት፡፡ ያ ግን ፀሀይ እስኪወጣ መጠበቅን ይጠይቃል፡፡ ህይወት ደግሞ እያንዳንዷን ቅፅበት ትፈልጋለች” ይላል ጐይቴ፡፡
ካለፉት የወረስነው፣ ወይም የወረስን የመሰለንን ነገር ልብ ብለን እንመርምር፡፡ ለህዝብ ሰጥተነዋል ያልነውን ነፃነት፣ የኢኮኖሚ ብልፅግና፣ ፍትሕ-ርእዕ፣ ዲሞክራሲና እኩልነት እንመርምር፡፡ ስትራቴጂ በነደፍን፣ መመሪያ ባወጣን፣ ሪፖርት ባቀረብን ቁጥር ምን ያህል ለህዝብ ጠቀመ? ከሚለው ማንፀሪያ አኳያ እናስተውለው፡፡ መለስ ብለን፤ ያለምነውን ነገር፣ እጅ-ካስገባነው ነገር እናወዳድር፡፡ አለበለዚያ፤ የማታ ማታ “የዝንጀሮ ልጅ ቅቤ ተቀብተህ ና ቢሉት፤ ቅቤ ቢኖር ያባቴ ታፋ ይህን ይመስል ነበር ወይ” አለ እንደሚባለው እንዳይሆን እናስብ፡፡

ለፓትትሪያርክነት ይታጫሉ ተብለው የተጠበቁ ሊቃነጳጳሳት አልተካተቱም
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ÷ በፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴው ተለይተውና ተጣርተው በሚቀርቡለት አምስት ዕጩ ፓትርያሪኮች ላይ ዛሬ መወያየት ይጀምራል፡፡
ለምልአተ ጉባኤው ስብሰባ በሀገር ውስጥና በውጭ የተመደቡ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የሚገኙ ሲኾን አስመራጭ ኮሚቴው ባወጣው የምርጫ መሪ ዕቅድ መሠረት፣ ለዕጩ ፓትርያሪክነት ይኹንታ ያገኙ አምስት ዕጩ ፓትርያሪኮች የካቲት 18 ቀን 2005 ዓ.ም ለሕዝቡ ይፋ የሚደረጉበት ውሳኔ የሚተላለፍበት ይኾናል፡፡
የፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴው ከቤተ ክርስቲያኒቱ ካህናትና ምእመናን የተገኙትን ጥቆማዎች እንደ ግብአት በመያዝና በፓትርያሪክ ምርጫ ሕጉ የሰፈረውን ድንጋጌ በመጠቀም እንደለያቸው የተነገሩትን ዕጩ ፓትርያሪኮች ዝርዝር ለቅ/ሲኖዶሱ የሚያስረክበው በዛሬው ዕለት እንደኾነም ታውቋል፡፡ ኮሚቴው የዕጩዎቹን ዝርዝር ለቅ/ሲኖዶሱ ከማቅረቡ ቀደም ብሎ የወጡ መረጃዎች በዕጩ ፓትርያሪክነት የተመረጡት አምስት ሊቃነ ጳጳሳት÷ በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማትያስ፣ የወላይታ ዳውሮ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፣ የባሌ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የከፋ ሸካ ቤንች ማጂ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል እንዲሁም የሰሜን ጎንደር ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ናቸው፡፡
በዕጩዎች ዝርዝር ውስጥ ለፓትርያርክነት ይበቃሉ ተብለው ከታሰቡት ሊቃነ ጳጳሳት÷ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል፣ ብፁዕ አቡነ ገብርኤል፣ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ እና ብፁዕ አቡነ ጎርጎሬዎስ መካከል የተወሰኑት አለመካተታቸው የምርጫውን ሂደት የሚከታተሉ አካላትን አነጋግሯል፡፡ አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች፣ የሚጠበቁት አባቶች በዝርዝሩ ላለመካተታቸው በምርጫው ዙሪያ ያሳስበናል የሚሉትን የቡድን እንቅስቃሴዎች በምክንያትነት ይጠቅሳሉ።

በዲያቆን ዳንኤል ክብረት በተደረሰው ”ጠጠሮቹ እና ሌሎችም ወጐች” የተሰኘ መፅሃፍ ላይ ነገ ከቀኑ 8 ሰዓት እስከ 11 ሰዓት በብሔራዊ ቤተመዘክር አዳራሽ ውይይት እንደሚካሄድ ሚዩዚክ ሜይዴይ አስታወቀ፡፡ ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ በማቅረብ የሚመሩት ሃያሲና ወግ ፀሐፊ መስፍን ሃብተማርያም ናቸው፡፡

 

ከትላንት በስቲያ በመላው ዓለም የተከበረውን የቫለንታይን (የፍቅረኞች ቀን) አስመልክቶ ነገ ከጧቱ ሦስት ሰዓት እስከ ቀኑ 10 ሰዓት በጃንሜዳ ፍቅረኛን በጀርባ አዝሎ ውድድር እንደሚያካሂድ “ኪዩፒድ” የማስታወቂያ ሥራ አስታወቀ፡፡ ውድድሩ ከ18 አመት በላይ የሆኑ ጥንዶች ብቻ እንደሚሳተፉ ታውቋል፡፡ ኪዩፒድ ከአዲስ አበባ አስተዳደር ስፖርት ኮሚሽን ጋር በመተባበር ባዘጋጀው ውድድር ላይ አስር ሺህ ጥንዶች ይገኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ድርጅቱ ገልጿል፡፡ “ልዩነታችን መወሰናችን” በሚል መሪ ቃል በሚካሄደው ውድድር ላይ ነፃ የኤችአይቪ ምርመራና የምክር አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን ፕሮግራሙ ሩጫ፣ እግር ኳስ፣ ጠረጴዛ ቴኒስና የኢትዮጵያ ባህላዊ ጨዋታዎች እንዲሁም የዘፈን ግብዣ እንደሚያካትት አዘጋጆቹ ጠቁመዋል፡፡

Saturday, 16 February 2013 13:50

“Eyes and Mist” ዛሬ ይመረቃል

ተስፋ በተጣለበት ፓን አፍሪካዊ ፀሐፊ ታሪኩ አባስ እቴነሽ የተፃፈው “Eyes and Mist” ኤክስፐርመንታል ረዥም ልቦለድ ዛሬ ምሽት በጁፒተር ኢንተርናሽናል ሆቴል እንደሚመረቅ አፍሪቅያህ ሚዲያና ኮሙኒኬሽን አስታወቀ፡፡ ልብወለዱ ጭብጡን በወቅቱ ተጨባጭ እውነታ ላይ በማድረግ በእንግሊዝኛ የተፃፈ እንደሆነ ታውቋል፡፡ በምረቃው ላይ በአዲስ አበባ የሚገኙ የውጭ ሀገር ዜጐች፣ ደራሲዎችና ሌሎች ታዋቂ ሰዎች እንደሚገኙ የሚጠበቅ ሲሆን መፅሐፉ በባህር ዳር እንዲሁም በሰርቢያ፣ አሜሪካና ቱርክ እንደሚመረቅም ለማወቅ ተችሏል፡፡

በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተውና በሊዛ ተሾመ የተደረሰው “ፍትህን በራሴ” ረዥም ልቦለድ መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ 248 ገፅ ያለው መፅሐፍ በሀገር ወስጥ 40.50 ብር፣ በውጭ ሀገራት ደግሞ 10 ዶላር እየተሸጠ ሲሆን ደሪሲዋ መታሰቢያቱን ለወሲብ ጥቃት ተጎጂዎች  አድርጋለች፡፡ መፅሐፉ በኢንተርናሽናል ሊደርሺፕ ኢንስቲትዩት ማተሚያ ቤት የታተመ ሲሆን  ደራሲዋ ካሁን ቀደም “አሜከላ ያደማው ፍቅር” የተሰኘ መፅሐፍ ለንባብ አብቅታለች፡፡

አሁን በህይወት በሌሉት ታዋቂው ገጣሚ ዮሐንስ አድማሱ የተዘጋጀው “የቀኝ ጌታ ዮፍታሔ ንጉሤ አጭር የሕይወቱና የጽሑፉ ታሪክ” የተሰኘ መጽሐፍ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመጻሕፍት ዝግጅት ተቋም የፊታችን ረቡዕ በ10፡30 በብሔራዊ ቴአትር እንደሚመረቅ ተገለፀ፡፡ መጽሐፉን የገጣሚ ዮሐንስ አድማሱ ወንድም የሆኑትና ባለፈው ሳምንት ሕይወታቸው ያለፈው ዶ/ር ዮናስ አድማሱ ኤዲት እንዳደረጉት ታውቋል፡፡ በመጽሐፉ ምረቃ ዕለት ከዮፍታሔ ንጉሤ ሥራዎች ተቀንጭበው የሚቀርቡ ሲሆን፤ ዮፍታሔ የደረሰውን “አፋጀሽኝ” ትያትርን ለመጀመሪያ ጊዜ የተወኑት አቶ በለጠ ገብሬ ይገኛሉ፡፡ ከአቶ በለጠ ሌላ አርቲስት ሃይማኖት አለሙ በመርሃ ግብር አስተዋዋቂነት፣ ደራሲና ሃያሲ አቶ አስፋው ዳምጤ እና ፕሮፌሰር ሺፈራው በቀለ ስለ መጽሐፉ አስተያየት፣ ፕሮፌሰር ማስረሻ ፈጠነ ስለ ሕትመቱ እንዲሁም ዶ/ር ያዕቆብ አርሳኖ ንግግር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

* ተቃዋሚዎች የመሰብሰቢያ አዳራሽ የሚያከራየን አጣን አሉ!
* የሆቴል ባለቤቶች “ለምን እንደጭራቅ ፈሩን” ብለው ራሳቸውን ይጠይቁ!

በተለያዩ ጊዜያት ከአገራችን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር የመገናኘትና ኢንተርቪው የማድረግ ውጤት አልባ ሙከራዬን በተመለከተ በማቀርባቸው መጣጥፎች የተነሳ አንድም ትላልቅ ባለስልጣናትን የማግኘት ከፍተኛ ረሃብ አሊያም ወደ ፖለቲካው ሙያ የመግባት ፅኑ ፍላጎት እንዳለኝ የሚያስቡ የዋሆች አይጠፉም ብዬ እገምታለሁ፡፡ (ሥራዬን በአቋራጭ ማመልከቻ እንደማስገባት እየቆጠሩት) እነሱ ይሄን ማሰባቸው ኃጢያት ነው የሚል አቋም ባይኖረኝም በመርህ ደረጃ ሃሳባቸው የአመለካከት ችግር ያለበት መሆኑን በማያዳግም መልኩ መንገር ተገቢ ነው ብዬ አምናለሁ (የኢህአዴግን መግለጫ መሰለ አይደል?) እናላችሁ --- ለእኒህ የዋሆች አንድ ቀልድ አዘል ቁምነገር ልነግራቸው ፈለግሁ (እንደኢህአዴግ መፈረጅ ስለማልወድ ነው!)
ከጥቂት ዓመታት በፊት የሆነ ነው፡፡ አንድ ወጣት ሚኒባስ ታክሲ ውስጥ ኀይሌ ገብረሥላሴ ወደ ፖለቲካው ሊያተኩር ነው የሚለውን ወሬ ጮክ ብሎ ለጓደኞቹ ያወራል፡፡ ከጓደኞቹ መካከል ይህንን ጨዋታ ከጎኑ ለተቀመጡ አዛውንት ሊያጋራ የፈለገው ወጣት ወደሳቸው ዞር ብሎ -
“ይህን ታሪክ ሰሙ አባባ?”
“የትኛውን?”
“ኃይሌ ገ/ሥላሴ “ሩጫውን ትቼ ፖለቲካው ላይ ላተኩር ነው የምፈልገው” አለ የተባለውን”
“ምን ነካው እሱ ደሞ ---- ከእውነት ወደ ውሸት ይሄዳል እንዴ?” ሲሉ ዘበቱ አዛውንቱ፡፡
መቼም የአገር ሽማግሌ አይጥፋ ነው (እንደ ኀይሌ የሚሰማ ሲገኝ ነዋ!) ይሄው ከዚያ ወዲህ ጀግናው አትሌታችን “ፖለቲካ ለምኔ!” በማለት ሙያው ላይ አተኩሮ በመትጋት ላይ ነው - እውነቱ ላይ ማለት ነው፡፡ ለነገሩማ የፖለቲካ ጠበኞች አስታራቂ ሽማግሌ ሆኖም አይቶታል - ፖለቲካ ውሸት (የዋሾዎች) መሆኑን፡፡
የ97 ምርጫን ፖለቲካዊ ቀውስ ተከትሎ፣ ከየቤታቸውና ቢሮአቸው ተለቃቅመው የታሰሩትን (ኢህአዴግ “ራሴን ከናዳ ለማዳን ነው ያሰርኳቸው” ብሏል!) የቅንጅት አመራሮች ለማስፈታት የተቋቋመው የአገር ሽማግሌዎች ኮሚቴ አባል እንደነበረም አይዘነጋም፡፡

(አንዳንድ በ97 ምርጫ የተዘረሩ የኢህአዴግ አባላት “ቅንጅት” የሚለውን ቃል ሲሰሙ ይበረግጋሉ የሚባለው እውነት ነው እንዴ?)
አትሌት ኃይሌ በሽምግልና ሰበብ ወደ ፖለቲከኞቹ መቅረቡ ትልቅ ተመክሮ ሳይሰጠው የቀረ አይመስለኝም - የሦስተኛ ዓለም ፖለቲካን እርም ለማለት!! (ሩጫ ነፃነት ይፈልጋል አቦ!) ይሄን ሁሉ ያመጣሁት መቼም ለምን እንደሆነ ሳትገነዘቡ አትቀሩም ብዬ አምናለሁ፡፡ እኔም ከኃይሌ ተምሬአለሁና ፖለቲከኛ ወይም ባለሥልጣን የመሆን ህልምና ምኞት የለኝም ልላችሁ ፈልጌ ነው (ፖለቲካ ኪሳራ እንጂ ትርፍ የለውም ያለው ማን ነበር?) ግን ደግሞ የአገሬ ጉዳይ ያገባኛልና ኪሳራ ቢሆንም ፖለቲካ ማውራቴ፣ ፖለቲከኛ ማማቴ (ሱስ እኮ አይደለም!) አይቀርም - ምርጫ ስለሌለኝ (ፖለቲካ እንጀራዬ ነዋ!)
“የአገሬ ጉዳይ ያገባኛል” የምትለዋ ሐረግ ምን እንዳስታወሰችኝ ታውቃላችሁ? የገጣሚ ኑረዲን ዒሳን “እኔ ምን አገባኝ” የምትል ግጥም!
እኔ ምን አገባኝ የምትሉት ሃረግ
እሱ ነው ሃገሬን ያረዳት እንደበግ
የሚል ግጥም ልፅፍ
ብድግ አልኩኝና
ምን አገባኝ ብዬ
ቁጭ አልኩ እንደገና፡፡
እኔ ግን በአገር ጉዳይ ምን አገባኝ ብሎ መቀመጥ አልፈጠረብኝም (ዕድል ይሆን ፍርጃ?) በነገራችሁ ላይ መቼና የት እንደሆነ ባላስታውስም የተከበሩ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ፣“በአገራችሁ ጉዳይ ምን አገባኝ አትበሉ!” የሚል ምክር የለገሱ መሰለኝ፡፡ አሁን እንግዲህ በርዕሴ ላይ እንደጠቆምኩት “ጠ/ሚኒስትሩን አነጋገርኳቸው!” ያልኩትን ጉዳይ ላብራራላችሁ፡፡
እውነቴን ነው የምላችሁ አዲሱ ጠ/ሚኒስትራችን (ግን ለምንድነው ሁሌ አዲስ የሚመስሉኝ?) የተከበሩ አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ እንደ ቱባ ባለሥልጣን (ያውም የአገር መሪ!) ፈፅሞ አይከብዱም፡፡ ፊታቸው ላይ የወዳጅነትና የፍቅር መንፈስ እንጂ የመጠራጠርና የተዓብዮ ስሜት አይታይባቸውም (ዓይኔ ይሆን እንዴ?) በእርግጥ ከዚህ ቀደም ከኢቴቪና ከአዲስ አበባ መስተዳድር ቴሌቪዥን ጋር ያደረጉትን ኢንተርቪው ስከታተል ተመሳሳይ ስሜት ተሰምቶኝ ነበር፡፡ በአጭሩ ምን ለማለት ፈልጌ መሰላችሁ? ባለሥልጣን ባለሥልጣን ሳይሆን ሰው ሰው የሚሸቱ ጠ/ሚኒስትር ሆኑብኝ ልል ፈልጌ ነው (ማን ይሆን “ሰዓሊ ከመሆንህ በፊት ሰው ነህ” ያለው?) ለምን እንደሆነ ባላውቅም ጠ/ሚኒስትሩ “ትንሽ ቆይተው----ሥልጣን ሲጥማቸው ይለወጣሉ” የሚል አጉል ጥርጣሬ አደረብኝ፡፡ የብዙ አፍሪካ አገራት መሪዎችን ታሪክ ስላነበብኩ ይሆን? (“before and after power” ታሪካቸውን ማለቴ ነው!) የአፍሪካ አምባገነን መሪዎችማ ቀላል ይለወጣሉ መሠላችሁ! (የሆሊውድ ፊልም ላይ እንዳለችው “ማያ” እኮ ነው እየተቀያየሩ ህዝባቸውን ግራ የሚያጋቡት - አንዴ ሰው ሌላ ጊዜ ወፍ፣ አንዴ ጉንዳን ሌላ ጊዜ ደግሞ ድመት እየሆኑ!) ብቻ አንድዬ ይጠብቀን!!
ፕሬዚዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር በቅርቡ ባደረጉት ልዩ ቃለምልልስ፣ “ከአሁኑና ከንጉሱ ዘመን የፓርላማ ሥርዓት ይበልጥ ነፃነት የሰፈነበት የትኛው ነው?” ሲባሉ፣ ሁለቱ ፓርላማዎች ለየቅል መሆናቸውን ገልፀው፣የአሁኑ “የፓርቲ ዲሲፕሊን” የሚባል ነገር ስላለ ለግለሰቡ “ፍፁም ነፃነት” የሚሰጥ አይደለም ብለዋል (የዲፕሎማሲ ችሎታቸውን ለአንዳንድ የኢህአዴግ አመራሮች ተመኘሁላቸው!) እናላችሁ----ይሄ “የፓርቲ ዲሲፕሊን” የሚሉት ክፉ አባዜ፣እኚህን “ሰው ሰው የሚሸቱ ጠ/ሚኒስትር” እንዳይለውጥብን ክፉኛ ሰጋሁ፡፡ (ፓርቲው የጠ/ሚኒስትርነት “ኩፍጥና” ያንሳቸዋል ብሎ ከገመገማቸው እኮ አለቀልን!)
እኔና እሳቸው በተገናኘንባት የጠ/ሚኒስትር የማትመስል ትንሽዬ ቢሮ ውስጥ ስንታይ፣ አንድ የአገር መሪና ዘወትር ከስጋት ተላቅቆ በማያውቅ የግል ፕሬስ ውስጥ የሚባትል ጋዜጠኛ አንመስልም ነበር፡፡ አስተማሪና ተማሪ እንጂ! በነገራችሁ ላይ የእንግሊዝኛ ጋዜጦቻችን አዲሱን ጠ/ሚኒስትር “ኃይሌ” በሚል አሳጥረው እንደሚጠሯቸው ያወቅሁት በቅርቡ ነው፡፡ እንግዲህ ዝርዝሩን ባላውቅም ከሳቸው ጋር የተገናኘሁት ከግል ፕሬስ ኢንተርቪው ለማድረግ “እጣ ወጥቶልኝ” እንደሆነ የሰማሁት ከአለቃዬ ነው፡፡ (“የፕሬስ ነፃነት በእጣ” የተባለ አይመስልም?) ከሁሉም ያልገባኝ ግን ምን መሰላችሁ? ለምን “አርነት የወጡ ሃሳቦች” የምትል ሚጢጢዬ የግጥም መፅሃፍ በእጄ እንደያዝኩ ነው፡፡ በእርግጥ ገጣሚውን ዳዊት ፀጋዬን በደንብ አውቀዋለሁ፡፡ የግጥሙን መፅሃፍም ፈርሞበት ነው ያበረከተልኝ፡፡ (ኢንተርቪው እንጂ የ“አርነት” ጥያቄ አቅርብ አልተባልኩ!) አልፎ አልፎ ፊትለፊቴ የተቀመጡትን ጠ/ሚኒስትር እየቃኘሁ፣በአብዛኛው ግን ግጥሞቹን ያለቀልቤ እያነበብኩ ሳለ ነው፣ ፕሮቶኮሏ ኢንተርቪውን እንድጀምር ምልክት የሰጠችኝ፡፡ በደመነፍስ መፅሃፍዋን ገልጬ “ለአንተ ስል”
የምትለዋን የዳዊት ግጥም ፈቃዳቸውን ሳልጠይቅ ላነብላቸው ተዘጋጀሁ (ምን ፈልጌ እንደሆነ ግን ለራሴም አልገባኝ!)ንባብ ከመጀመሬ በፊት ቀና ብዬ የጠ/ሚኒስትሩን በመነፅር የተከለሉ ዓይኖች ቃኘት አደረግሁ - የደስታ ብርሃን ይረጫሉ፡፡ ቢያንስ ግጥም እንደማይጠሉ ገባኝ (በሆዴ“አቦ ይመችዎት!” ያልኩኝ መሰለኝ)
ሰዎች በረሃብ ሲያልቁ
አፋቸውን በአንተ እንዳያላቅቁ
ፍትህ በምድር ሲጠፋ
ብስጭታቸው እንዳይከፋ
እምነታቸው እንዳይላላ
ነፍሳቸው አንተን እንዳትጠላ፣
“እግዚአብሄር የለም እንዴ?” ሲሉ
“አዎ የለም” የምለው
ስለ አንተ ብዬ ነው፡፡
ቀና ብዬ ሳያቸው መሳቅ ፈልገው ራሳቸውን የገደቡ ዓይነት ስሜት አነበብኩባቸው - ገፅታቸው ላይ፡፡ ግን ለምን በነፃነት አልሳቁም? (ሺ ዓመት አይኖር!) ትዝ ይላችኋል---- የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር (ነፍሳቸውን ይማረውና!) በሚሊኒየም በዓል ላይ ሚሊኒየም አዳራሽ ውስጥ ከባለቤታቸው ጋር በሱዳንኛ ዘፈን ሲደንሱ? ለምን እንደሆነ አላውቅም፣የዛን ዕለት ደስ ብሎኝ ነበር፡፡ ለጠ/ሚኒስትሩ ሌላ ግጥም ልደግምላቸው ከጅሎኝ ነበር፡፡ (ነፍሴ first thing first ያለችኝ መሰለኝ) በእርግጥ እሳቸውም ሁለተኛ ግጥም እንዲነበብላቸው የፈለጉ ይመስላሉ፡፡ (ጥያቄው በግጥም ንባብ እንዲቀየርላቸው ተመኝተው ይሆን እንዴ?) እውነት ለመናገር ግን በደስታ ስሜት ተጥለቅልቄ ነበር! (ግጥም ይወዳሉ ማለት ነው አልኩ - ለራሴ እየደጋገምኩ!) ግን ለምን ደስ አለኝ? “ግጥም መውደድና አለመውደድ ከባለሥልጣን ሥራና ባህርይ ጋር የሚያገናኘው ነገር የለም” የሚል ሃሳብ ድንገት ወደአዕምሮዬ መጣብኝና ደስታዬን ከመቅፅበት ነጠቀኝ- ምቀኛ! ሃሳቡ እንኳን ስህተት ያለው አይመስልም፡፡ አምባገነን መሪ ምን ግጥም ቢወድ እኮ ከአምባገነንነቱ ላይ አይቀንስለትም! (ግጥም ሰብዓዊነት ያላብሳል ያለው ማነው?) ለነገሩ ከኢህአዴግም ከተቃዋሚዎችም ስንት ባለቅኔ ፖለቲከኞች እኮ አይተናል፡፡ (ቅኔ መቀኘትና ዲሞክራሲን መቀኘት ግን ለየቅል ናቸው!)
ለአይን መግለጫ ያህል አንዷ ግጥም በቂ እንደሆነች በማሰብ በቀጥታ ወደ ጥያቄዎቼ ለመግባት ወሰንኩ፡፡

እሳቸውም ፈተና እንደሚጠባበቅ ትጉህ ተማሪ በትኩረት እየተጠባበቁኝ ነበር፡፡ ለነገሩ የ87 ሚ. ህዝብ ህልቆ መሳፍርት ጥያቄዎችን መመለስ ከየትኛውም ምድራዊ ፈተና የበለጠ ሊከብድ እንደሚችል ለማወቅ “ኒዩክለር ሳይንስ ማጥናት” አይጠይቅም፡፡ በተለይ ከድህነት ለመላቀቅ መከራዋን በመብላት ላይ ያለች ምስኪን አገር የመምራት ሃላፊነት ድንገት ትከሻው ላይ ለወደቀበት “የዩኒቨርስቲ ምሁር”!!
ከጃኬቴ ኪስ ውስጥ ያወጣሁትን ማስታወሻ ደብተር ገልጬ፣ጠ/ሚኒስትሩ በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ ባሉ ቁጥር “የመለስን ራዕይ እናሳካለን” በማለት እንደፀሎት የሚደጋግሙትን ትክት ያለ ንግግር የተመለከተ ጥያቄዬን በማስቀደም ቃለምልልሱን አሃዱ ልል ወደድኩ፡፡
ክቡር ጠ/ሚኒስትር፤አንዳንድ የህብረተሰብ ወገኖች ጠ/ሚኒስትሩ ትክክለኛ ራሳቸውን ሆነው የምናያቸው መቼ ነው ሲሉ ይደመጣሉ (ጠ/ሚኒስትሩ አምልጧቸው ሳቅ አሉ) እውነቴ ነው ጠ/ሚኒስትር… ሁልጊዜ ሲናገሩ የቀድሞውን ጠ/ሚኒስትር ንግግር ከማስታወስና “የመለስን ሌጋሲ እናስቀጥላለን!” ከማለት ውጭ የራስዎትን አቋም የሚያንፀባርቅ ነገር ተናግረው አያውቁም፡፡ እንደውም ዳያስፖራ ያሉ ተቃዋሚዎች፤የምዕራቡ ዓለም “ጐስት ራይተር” ሲሉ ሰምታ ኢትዮጵያም “ጐስት ፕራይም ሚኒስትር” ፈጠረች እያሉ እንደሚቀልዱ ሰምቻለሁ… በዚህ ጉዳይ ላይ ማብራርያ ቢሰጡ ጥሩ ይመስለኛል…
(ጠ/ሚኒስትሩ እንደገመትኩት የስሜት ለውጥ አላሳዩም፤ ዘና ብለው መመለስ ጀመሩ፤ጥያቄዬ ቀድሞ ደርሷቸው ይሆን እንዴ? አልኩ - ለራሴ፡፡ ግን እንዴት ሆኖ? ወዲያው ትኩረቴን ወደመልሳቸው አደረኩኝ) ማንም ምንም ቢል የሚለወጥ ነገር የለም፡፡ አሁንም ወደፊትም የመለስን ሌጋሲ ነው የምናስቀጥለው፡፡ ፓርቲው ለዚህ ትግል ሲመርጠኝ የመለስንና የፓርቲያችንን ራዕይ ከጓዶቼ ጋር ሆኜ እውን ለማድረግ ነው ቃል የገባሁት፡፡ ከዚህ የበለጠም ሆነ ከዚህ ያነሰ አይደለም የእኔ ሚና፡፡ የአገርና የፓርቲ ራዕይ ግለሰቦች በተቀያየሩ ቁጥር የሚቀያየር አይደለም፡፡ ጉዳዩን በዚህ መልኩ ብናየው ሳይሻል አይቀርም (እንዴ---በየት መልኩ?) (ቀጣዩን ጥያቄ አስከተልኩ) በቅርቡ “ጅሃዳዊ ሐልካት” የተሰኘ በአክራሪነት ዙርያ ያጠነጠነ ዶክመንታሪ በኢቴቪ ሲሰራጭ እንኳን፣የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር ንግግር ነው የተደመጠው፡፡ ይሄ ደግሞ በህብረተሰቡ ዘንድ ብዥታ ፈጥሯል፡፡ ይሄን ብዥታ ማጥራት የሚገባ አይመስልዎትም?
ምንም ብዥታ የለም፣ ሁሉም ነገር ጥርት ያለ ነው፡፡ በሁሉም ረገድ ሌጋሲውን የማስቀጠል ዓላማ ይዤ ነው የምንቀሳቀሰው፡፡ ፓርቲውም ለትግል ያጨኝ ይህን አደራ እንድወጣ ብቻ ነው (መልሳቸውን በአጭሩ ገቱት)
አሁን ደግሞ ወደ ተቃዋሚዎች እናምራ -------- ራሳቸውን ከምርጫው ያገለሉ 28 ተቃዋሚ ፓርቲዎች ህዝባዊ ስብሰባ ለማድረግ ፈቃድ አግኝተው፣15 ሆቴሎች አዳራሽ አናከራይም በማለታቸው የምንሰበሰብበት አጥተናል የሚል ቅሬታ ማቅረባቸውን ሳይሰሙ የቀሩ አይመስለኝም------
(ቅንነት የጎደላት የምትመስል ፈገግታ ብልጭ አደረጉና መናገር ጀመሩ) ቅሬታውን እንኳ አልሰማሁትም… እኔ የማውቀው የማተምያ ቤቶቹን ብቻ ነው፡፡ እሱን አንተም እንደምታውቀው፣ነፃ አገር ውስጥ እንደምንኖርና ማንኛውም ባለስልጣን ቢሆን ማተምያ ቤት ደውሎ የ“አንድነት” ጋዜጣን አታትሙ የማለት መብት እንደሌለው ገልጬ፣ነገሩ በዚያው ተቋጭቷል፡፡ የአዳራሹን እንኳን ይሄው ካንተ መስማቴ ነው፡ክቡር ጠ/ሚኒስትር፤ የማተምያ ቤቶቹ ችግር እኮ እርስዎ እንደሚሉት አልተቋጨም፡፡ አንድነት ፓርቲ እንደውም የራሱን ማተምያ ቤት ለማቋቋም የገንዘብ ማሰባሰብያ (Fundraising) ፕሮግራም ሰሞኑን ማዘጋጀት ጀምሯል፡፡
ኤክሰለንት! ፓርቲዎቻችን እንዲህ ችግር ፈቺ ነው መሆን ያለባቸው፡፡ ኢህአዴግም ሊያግዛቸው ይችላል፡፡ ያው ለአገሪቱ የመድበለ ፓርቲ ስርአት መጠናከር አነሰም በዛም አስተዋፅኦ እንዳላቸው ፓርቲያችን ያምናል፣ ስለዚህ ነገሩን የዲሞክራሲ ሥርዓትን እንደማጎልበት በመቁጠር የማተምያ ማሽኑ ከቀረጥ ነፃ እንዲገባ እናግዛቸዋለን፡፡
(ጆሮዬ የሚሰማውን ማመን አቃተው) ይሄ ደስ የሚል ሃሳብ ነው ጠ/ሚኒስትር--- ገዢው ፓርቲና ተቃዋሚዎች በትብብር ቢሰሩ እኮ ጥቅሙ ለአገር ነው… (ሆኖም አላስጨረሱኝም) በትብብር መስራት የሚለው እንኳ አያስኬድም፡፡ የኢህአዴግና የተቃዋሚው መስመር ፈፅሞ የሚገናኝ አይደለም፡፡ ጉዞአችን ለየቅል ነው፡፡ ኢህአዴግ የጠራ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ አቅጣጫን ነው የሚከተለው፡፡ በዚህ ሂደት ደሞ ኪራይ ሰብሳቢዎችን በየጣቢያው እያራገፈ፣ ልማታዊ ኃይሎችን አቅፎና ደግፎ ነው ወደ ግቡ የሚደርሰው፡፡ ስለዚህ ከተቃዋሚዎች ጋር የሚያስተባብረን የጋራ ዓላማ የለንም፡፡ በመርህ ደረጃ ግን ህዝቡ አማራጭ እንዳያጣ የተቃዋሚዎችን መኖር እንደግፋለን (ኢህአዴግን ያመነ አልኩ - በሆዴ!) እሺ የሆቴል መሰብሰቢያ አዳራሽ አጣን ለሚሉት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ምን መፍትሄ ይሰጧቸዋል? (በተስፋ መቁረጥ ስሜት ነው የጠየቅኋቸው)
ዌል… ኢህአዴግ እንግዲህ ሆቴልም አዳራሽም የለውም፡፡ ምናልባት እነ መድረክ እንደ ጦር የፈሩትን የምርጫ ስነምግባር ደንቡን ለመፈረም ፈቃደኛ ከሆኑ፣ በፓርቲዎች የጋራ ምክክር መድረክ በጉዳዩ ላይ ተወያይተን መፍትሄ ልንፈልግለት እንችላለን ብዬ አስባለሁ፡፡
ክቡር ጠ/ሚኒስትር፤ ፓርቲዎቹ እኮ ከህዝብ ጋር መገናኘት አልቻልንም… ሆቴሎች በአድማ አናከራይም ብለውናል… እንደውም የመንግሥት እጅ አለበት እያሉ ነው…
አሁንም ስለማተምያ ቤቶች ስናገር ያልኩትን እደግመዋለሁ፡፡ እኛ ሆቴሎችን እየዞርን “ለመድረክ ፓርቲ አዳራሽ አከራዩ አታከራዩ” እያልን እጃቸውን መጠምዘዝ አንችልም፡፡ መብትም የለንም፡፡ ዲሞክራሲያዊ አገር ውስጥ እኮ ነው ያለነው፡፡ ግን ፓርቲዎቹ፤ “እነዚህ ሁሉ ሆቴሎቹ ለምን እንደ ጭራቅ ፈሩን?” ብለው ራሳቸውን መጠየቅ ያለባቸው ይመስለኛል፡፡ ቆይ ለምን ፈሯቸው? እኔ የተቃዋሚ አመራር ብሆን ኖሮ ምክንያቱን ለማስጠናት እሞክር ነበር… ይሄ እኮ ስር የሰደደ ችግር ነው፡፡ ኢህአዴግ ለምሳሌ እንኳንስ የሆቴል አዳራሽ ኪራይ ሊከለከል ቀርቶ፤“የህዝብ ፓርቲ ስለሆነ ክፍያ አንቀበልም” በሚሉ የሆቴል ባለቤቶች ነው የተቸገረው፡፡ በርካታ አዳዲስ ባለአምስት ኮከብ ሆቴሎች አዳራሻቸውን በነፃ እንድንጠቀም እየጎተጎቱን ነው፡፡
ክቡር ጠ/ሚኒስትር፤ ስልጣን ላይ ያለ ፓርቲና ተቃዋሚ አንድ ሊሆን አይችልም--ተቃዋሚዎች እንደሚሉት፤ በ97 ምርጫ የግል ባለሃብት በሆኑ ደጋፊዎቻቸው ላይ መንግስት በፈፀመው ማስፈራሪያና ወከባ ባለሃብቶች በግልፅ ተቃዋሚዎችን ለመደገፍና ለማገዝ ይፈራሉ ይባላል፡፡ ይሄ ችግር እንዴት ይፈታል ብለው ያስባሉ?
መፍትሄው አንድ ብቻ ነው፤ተቃዋሚዎች እንደ ኢህአዴግ ህዝባዊ ፓርቲ መሆን አለባቸው፡፡ ኢህአዴግ የማተምያ ቤትና የስብሰባ አዳራሽ ችግር የማይገጥመው ገዢ ፓርቲ በመሆኑ አይደለም፤ ሰፊ ህዝባዊ መሰረት ያለው ልማታዊ ፓርቲ ስለሆነ ነው፡፡ (በዚህ ጉዳይ ላይ ከኢህአዴግ ጋር ሙግት መግጠም ጊዜ ማባከን ስለመሰለኝ አንድ ሁለት ከምርጫ ጋር የተገናኙ ጥያቄዎች ላቀርብላቸው ወሰንኩ)
…በሚያዝያ ወር ከሚካሄደው የአዲስ አበባና አካባቢ ምርጫ ጋር በተገናኘ የኢህአዴግ ፅ/ቤት ሃላፊ የሆኑት አቶ ሬድዋን ሰይድ “ተቃዋሚዎች ቢኖሩም ባይኖሩም ትርፍም ኪሳራም የላቸውም” ሲሉ በመናገራቸው በተቃዋሚዎች ጎራ ከፍተኛ ቁጣና ቅሬታ ቀስቅሷል፡፡

የሞባይሌ ድንገተኛ ጩኸት ከተቀመጥኩበት አስፈንጥሮ ሊያስነሳኝ ምንም አልቀረውም ነበር፡፡ በዚያ ላይ ሞባይሉ የትኛው ኪሴ ውስጥ እንደተሰወረ አላውቅም፤አጣሁት - ግን ጩኸቱን ቀጥሏል፡፡ ኪሴዬን በርብሬ በርብሬ ቀና ስል ጠ/ሚኒስትሩ የሉም፡፡ እሳቸው ብቻ ሳይሆኑ መቀመጫቸውም የለም፡፡ እኔና እሳቸው የነበርንበት ጠባብ ቢሮም ራሱ የለም፡፡ እኔም ያለሁት ወንበር ላይ ሳይሆን አልጋዬ ላይ ነኝ - መኝታ ክፍሌ ውስጥ! ሁለተኛውን ትራስ “አርነት የወጡ ሃሳቦች” የምትለዋ የግጥም መፅሃፍ የተንተራሰች መስላ ተቀምጣለች፡፡ ከግል ፕሬሶች መካከል “ዕጣ ደርሶኝ” ጠ/ሚኒስትሩን ኢንተርቪው ላደርጋቸው ቢሮአቸው መግባቴ በእውኔ ሳይሆን በህልሜ እንደነበር የተገነዘብኩት ዘግይቼ ነው፡፡ ከጠ/ሚኒስትሩ ጋር በህልሜ የጀመርኩትን ቃለምልልስ ሳልጨርስ ከመባነኔ የበለጠ ያናደደኝ ግን ላነብላቸው ያሰብኩትን ወሳኝ ግጥም ባለማንበቤ ነው፡፡ በህልምም ቢሆን ባነብላቸው ይሻል ነበር ብዬ ተፀፀትኩ፡፡ ከዚያም መፅሃፊቱን ጐተት አድርጌ እንደዘበት ገለጥ አደረግኋት - ልክ የታዘዘ ይመስል ገፅ 35 ለእሳቸው ያሰብኩት ግጥም ላይ አረፍኩ - “ህዝብ፣ እግዜር፣ መንግስት!” ይላል ርእሱ፡፡
እግዚአብሄር፣
ምን ብሎ ይመልስ የህዝብን እሮሮ?
መንግስትን፣
እንዲናገር እንጂ እንዳይሰማ ፈጥሮ!
ጠ/ሚኒስትሩ እቺን ግጥም ቢሰሙ ምን አይነት ስሜት ይፈጠርባቸው ይሆን? (በህልም አለምም ቢሆን ማለቴ ነው!)