Administrator

Administrator

ባለፈው ሳምንት በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት አካባቢ በርካታ ወጣቶች “ጉራማይሌ ቋንቋ፣ ጉራማይሌ ማንነት ይሆናል” የሚል ጥቅስ የታተመበት፤ ወይንጠጅ ቀለም ያለው ተመሳሳይ ቲሸርት ለብሰው በጋራ ሲጓዙ ትኩረቴን ሳቡት። እኔ ብቻ ሳልሆን ሌሎች መንገደኞችም በነገሩ መሳባቸው አልቀረም፡፡ አንዳንዶች እንደውም ቀረብ ብለው ሲጠይቁ ሰምቻለሁ፡፡ ለመሆኑ ቲ-ሸርቱ ላይ የሰፈረው ጥቅስ መልዕክት ምንድነው? ሃሳቡን ካመነጩት ስድስት ወጣቶች ጋር ጋዜጠኛ ብርሃኑ ሰሙ ቃለምልልስ አድርጓል፡፡ በቲ-ሸርት ላይ መልእክት ለማስተላለፍ መነሻና ምክንያት የሆናችሁ ምንድነው? የኮተቤ መምህራን ትምህርት ኮሌጅ የማታ ተማሪዎች ነን፡፡

በኢትዮጵያ ቋንቋዎች ትምህርት ክፍል ለሦስት ዓመታት የተሰጠንን የአማርኛ ቋንቋ አጠናቀን የዚህ አመት ተመራቂዎች ስለሆንን ደስታችንን በምን እናድምቅው ብለን ስናስብ፣ በአማርኛ ቋንቋ ዙሪያ የሚታይ ችግርን የሚያመለክትና የሚያወያይ መልእክት ማስተላለፍ ስለፈለግን “ጉራማይሌ ቋንቋ፣ ጉራማይሌ ማንነት ይሆናል” የሚል ጥቅስ በቲ-ሸርት ላይ አሳትመን በመልበስ እየተንቀሳቀስን ነው፡፡ ምን ያህል ተማሪዎች ናችሁ ለዚህ ዓላማ በጋራ እየተንቀሳቀሳችሁ ያላችሁት? በእኛ ዲፓርትመንት በማታው ክፍለ ጊዜ የምንማር ተማሪዎች ብዛት 116 ስንሆን በሦስት የተለያዩ ክፍሎች ነው የምንማረው፡፡ በምረቃችን ዋዜማ በጥቅስ መልእክት የማስተላለፉ ሀሳብ የመነጨው በአንደኛው ክፍል በምንገኝ ስድስት ጓደኛሞች ቢሆንም አሁን ሁሉም የማታው ክፍለ ጊዜ ተመራቂ ተማሪዎች ደግፈውት በጋራ እየተንቀሳቀስን ነው፡፡ አማርኛ ቋንቋ ላይ ተጋርጧል የምትሉት ችግር ምንድነው? ቋንቋው ላይ ችግር ተከስቷል ብለን ግንዛቤ ለማስጨበጥ በጋራ እየተንቀሳቀስን ካለነው ተመራቂ ተማሪዎች መሀል አንዳንዶቻችን በግልም፣ በመንግሥትም ትምህርት ቤቶች ስለምናስተምር በተግባር ብዙ ችግር በየእለቱ እናያለን፡፡

ተማሪዎች በትምህርት ቤት ግቢ ወስጥ አማርኛ ቋንቋ እንዳይናገሩ የሚከለክሉ ትምህርት ቤቶች አሉ፡፡ በአማርኛ ቋንቋ የሚናገር ተማሪ ሀፍረት እንዲሰማው የሚያደርግ ተግባር ሲፈፀምባቸው ይታያል፡፡ አማርኛ ቋንቋ ከትምህርት ቤቱ ግቢ በ200 ሜትር ርቀት ብቻ ነው መናገር የሚቻለው የሚል ሕግ ያወጡ ትምህርት ቤቶችም አሉ፡፡ ወላጆች የትኛው ትምህርት ቤት ነው እንግሊዝኛ ጥሩ የሚያስተምረው እያሉ ነው ልጆቻቸውን ወደ ትምህርት ቤት የሚያስገቡት፡፡ ይህ ልማድ በጊዜ ካልተቀጨ በጥቂት አመታት ውስጥ ወጣቶች ለማንነት ቀውስ ችግር መጋለጣቸው አይቀርም፡፡ ይህ አደጋ መነጋገሪያ እንዲሆን በመሻት ነው እኛም ጥቅሱን አሳትመን በመልበስ በመንቀሳቀስ ላይ ያለነው፡፡ ቋንቋው በንግግር ብቻ ሳይሆን ለፅሁፍም ከማገልገሉ ጋር በተያያዘ ተከስቷል የምትሉት ችግር አለ? አማርኛ፤ እንግሊዝኛ ቋንቋ እያሳደረበት ባለው ጫና ምክንያት ለችግር መጋለጡን ለሕብረተሰቡ እያመለከቱ ያሉ ሌሎች አካላትም አሉ፡፡ በኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙሃን የቋንቋ አጠቃቀም ዙሪያ በጌታቸው በልዩ የተሰራ ጥናት አለ፡፡

ከሌሎች የአገራችን ቋንቋዎች በተሻለ ሁኔታም በአማርኛ ቋንቋ ዙሪያ ብዙ ጥናት ተሰርቷል፡፡ እንዲህም ሆኖ የአውሮፓውያን አስተሳሰብ በተለያየ መልኩ ጫና እያሳደረብን እንዳለው ሁሉ፣ ቋንቋችን ዋነኛው ሰለባ እየሆነ መምጣቱ በትምህርት ቤቶች ብቻ ሳይሆን በተለያዩ እለታዊ እንቅስቃሴዎቻችን ውስጥ ይታያል፡፡ “ጉራማይሌ ቋንቋ፣ ጉራማይሌ ማንነት ይሆናል” የሚለው መልእክታችን አማርኛ ቋንቋን ማዕከል ያደረገ ቢሆንም ሌሎች የአገራችን ቋንቋዎችንም ይመለከታል፡፡ ቋንቋ መግባቢያ ብቻ ሳይሆን ባህል፣ እምነት፣ ወግ፣ ልማድ፣ መከባበር፣ መተሳሰብ፣ ሀዘን ደስታ… መግለጫ ነው፡፡ የራስን ቋንቋ እንደሚገባው አለማወቅ ለማንነት ቀውስ ችግር ይዳርጋል የምንለው ለዚህ ነው፡፡ አማርኛ የፌደራሉ መንግሥት የሥራ ቋንቋ ነው፡፡ በአገራችን ልጆች አፋቸውን በፈቱበት ቋንቋ እንዲማሩ ተወስኗል፡፡ በአዲስ አበባ የሚወለድ ልጅ አፉን የሚፈታው በአማርኛ ቢሆንም በትምህርት ቤቶች ግን በእንግሊዝኛ ቋንቋ የላቀ ችሎታ እንዲኖረው እየተሰራ ወይም የወላጆች ፍላጐት እንደዚያ እንዲሆን የመፈለግ አዝማሚያ በስፋት ይታያል፡፡ ይህ ጅማሬ በዚሁ መልኩ እያደገ ከሄደ በማንነታችን ላይ ጉዳት ማስከተሉ አይቀርም፡፡

በየእለቱ ቅላፄያቸው ወደ እንግሊዝኛ ቋንቋ የተለወጡ የአማርኛ ቃላትን እንሰማለን፡፡ በሙዚቃችን ውስጥ እንዲህ አይነቱ ነገር እየበዛ መጥቷል፡፡ የተማሩ የሚባሉ ሰዎች ብቻ ሳይሆኑ ፊደል ያልቆጠሩ እናቶቻችንም በንግግሮቻቸው መሀል ብዙ የእንግሊዝኛ ቃላት ሲጠቀሙ እየሰማን ነው፡፡ ቋንቋ የሚፈጠረውና የሚያድገው አንዱ ከሌላው እየወሰደና እየሰጠ ስለሆነ እንዲህ መሆኑ ምን ይገርማል? ችግሩ መቀባበሉ ላይ ሳይሆን አወሳሰዱ ላይ ነው፡፡ ሁሉም ቋንቋ ሀሳብን ለመግለፅ በራሱ ምሉዕ ነው ተብሎ ይታመናል፡፡ አማርኛ ቋንቋ በአባባል፣ በተረት፣ በእንቆቅልሽ፣ በሥነቃል የዳበረና ሀሳብን ለመግለፅ ምንም ችግር የሌለበት ሆኖ ሳለ፣ በንግግር መሐል እንግሊዝኛ ቃላትን መጠቀም አዋቂና የተማረ ያሰኛል ስለሚባል፤ ፋይዳቸው ምንም የሆነ የእንግሊዝኛ ቃላት በአማርኛ መሀል መጨመር ተለምዷል፡፡ ለምሳሌ ተማሪዎቻችንን ለፈተና እየተዘጋጃችሁ ነው? ብለን ስንጠይቃቸው “ዌል ዝግጁ ነን” የሚል መልስ ይሰጡናል፡፡ በዚህ መልስ ውስጥ “ዌል” የሚለው የእንግሊዝኛ ቃል መጨመሩ ያስገኘው ምንም ጥቅም የለም፡፡ በአማርኛ ቋንቋ ውስጥ ከሌሎች ቋንቋዎች ወስደን የምንገለገልባቸው ብዙ ቃላት አሉ፡፡ ቴሌቪዥንና ሬዲዮ የሚሉትን ቃላት እንደምሳሌ መጥቀስ እንችላለን፡፡

የቴክኖሎጂ ስያሜዎች ወደ አገራችን ሲገቡ በአገራችን አባባል የሚተረጉም አካል አለመኖሩ ለችግሩ የራሱ የሆነ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ ለምሳሌ ጀርመኖች የቴክኖሎጂ ቃላትን በራሳቸው አባባል ተርጉመው የቋንቋቸው አካል ያደርጋሉ፡፡ በእኛ አገር ሲሆን የሚታየው ግን ከዚህ በተቃራኒ ነው፡፡ ከቴክኖሎጂ ማደግ ጋር የሚፈጠሩ ስያሜዎች በየእለቱ ወደ ቋንቋዎቻችን ይገባሉ። ከዚህም ባሻገር ከበድ ያሉ ፅንሰ ሀሳቦችን ተጨማሪ ማብራሪያ ለማያስፈልጋቸው አባባልና አገላለፆች ሁሉ የእንግሊዝኛ ቃላትን መጠቀም እየበዛ መጥቷል፡፡ የተቀላቀለ ቋንቋ የሚናገር ሰው በበዛ ቁጥር ቅይጥ ማንነት ያላቸው ሰዎች ይበረክታሉ፡፡ የአማርኛ ቋንቋም የመጥፋት አደጋ እንደተጋረጠበት ይነገራል፡፡ በእኛም አገር “እንግአማ” ላይ ይወድቃል፡፡ ሂንዱ የሚባለው የሕንዶች ቋንቋ በእንግሊዝኛ ተፅእኖ ስር ወድቆ የመጥፋት አደጋ እየተፈጠረ ስለሆነ “ሳይቃጠል በቅጠል” እንደሚባለው መፍጠን ይኖርብናል፡፡ “እንግአማ” ምንድነው? እንግሊዝኛና አማርኛ ከሚሉት ሁለት ቃላት ተውጣጥቶ የተገኘ ቃል ሲሆን በሁለቱ ቃላት የተመሰረተ አዲስ ቋንቋ ለማለት ነው፡፡ አንድ ሰው ሁለት ማንነት ሊኖረው አይችልም፡፡ “እንግአማ” ሁለት ማንነት ይፈጥራል፡፡ አማርኛ ቋንቋ በዘይቤ የወሎ፣ የጐንደር፣ የጐጃም፣ የሰሜን እና የሸዋ በሚል በአምስት የተለያዩ ክፍሎች ይመደባል፡፡ የገጠር አማርኛ ተናጋሪዎች ሁሉ የእንግሊዝኛ ቃላትን እየደረቱ ሲጠቀሙ መስማት ተለምዷል፡፡ ቋንቋችን ጉራማይሌ ከሆነ ማንነታችንም ጉራማይሌ ይሆናል። አንድ የሬዲዮ ጋዜጠኛ “Part of the body” የሚለውን የእንግሊዝኛ ሐረግ ተናግሮ አብሮት ለሚወያየው የሥራ ባልደረባው “በአማርኛ ምንድነው የሚባለው?” ብሎ ትርጉም ሲጠይቀው ሰምተናል፡፡

ችግሩ እስከዚህ ድረስ ሰፍቶ የሚታይ ነው፡፡ እኛ እንግሊዝኛ ቋንቋን እያጥላላን አይደለም። እንግሊዝኛን ማወቅ የለብንም አላልንም። እንግሊዝኛን ብቻ ሳይሆን ሌሎች የአገርና የዓለም ቋንቋዎችንም ማወቅ ብንችል አንጐዳም፡፡ ማንነታችን ላይ ቆመን ሌላውን ለማወቅ ካልጣርን ግን ጉራማይሌ ማንነት ነው የሚኖረን፡፡ በአገር ውስጥ በሌሎች ቋንቋዎች ጫና ምክንያት ጉዳት ሲደርስበት የሚከላከልለት የሌለ የሚመስለው አማርኛ ቋንቋ፤ አሜሪካንን በመሳሰሉ ኢትዮጵያዊያን በብዛት በሚኖሩባቸው አገራት እንግሊዝኛን አሸንፎ ለመነጋገሪያነት መዋሉን እንሰማለን፡፡ ቻይናም በአገሯ በዩኒቨርስቲ ደረጃ ዜጐቿ እንዲማሩ እያደረገች ነው፡፡ ሌሎች ይህን ያህል ዋጋ ከሰጡት እኛ ከነሱ በላይ ልናከብረውና ልንጠነቀቅለት ይገባል፡፡ የአማርኛ ቋንቋ ትምህርት በአገር ውስጥ በተለያዩ የትምህርት ተቋማት ይሰጣል፡፡ የተለያዩ መፃህፍትም ይታተማሉ፡፡ ቋንቋውን ለመጠበቅና ለማዳን በተለይ ሕብረተሰቡን ማዕከል ያደረገ ሰፊ ሥራ መሰራት ይኖርበታል፡፡ ለዓላማችሁ ድጋፉን የሰጠ ማን አለ? ተቃውሞስ አልገጠማችሁም? ያለውን አደጋ መከላከል የሚያስችል ግንዛቤ ለማስጨበጥ ስንነሳ መምህር ደብሬ “ጉራማይሌ ቋንቋ፣ ጉራማይሌ ማንነት ይሆናል” የሚለውን ጥቅስ በመስጠት ተባብራናለች፡፡

መምህር የሻው ተሰማን መሰል መምህራንም ጥሩ ነው በማለት አበረታተውናል፡፡ ጥቅስ የታተመበትን ቲ-ሸርት ለብሰን በየአደባባዩ ስንንቀሳቀስ የሚያዩን ሰዎች ዓላማችንን እየጠየቁን ስንነግራቸው እንድንበረታና ሀሳቡን ለሚመለከታቸው አካላት እንድናደርስ በርቱ ይሉናል፡፡ ተቃውሞ ግን እስካሁን አልገጠመንም፡፡ ተመርቃችሁ ከወጣችሁ በኋላስ ለዚህ ዓላማችሁ ለመንቀሳቀስ ምን እድልና ተስፋ አላችሁ? አብዛኞቻችን አስተማሪ ስለምንሆን በተማሪዎቻችንና በትምህርት ቤታችን አካባቢ የምንሰራው ነገር ይኖራል፡፡ ስብስባችንም ሳይበታተን ለዚሁ ዓላማ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር የእግር ጉዞን መሰል የቅስቀሳ መድረኮች የማሰናዳትም እቅድ አለን። የምረቃችንን ዋዜማ በጭፈራና ሆይ ሆይታ ሳይሆን እንዲህ ባለ ቁምነገር ላይ ማሳለፋችንም እያስደሰተን ነው፡፡

“ዓለምን የቸገራት ምንድን ነው? ምግብ? ልብስ? ቤት? አዎን፤ በሙሉም ባይሆን በከፊል የነዚህ ነገሮች ችግር አለባት፡፡ …ነገር ግን እስካሁን ድረስ መድኃኒት ያልተገኘለት ችግር የመልካም ሰዎች ማነስ ነው” ይላል አቤ መስከረም 10 ቀን 1957 ዓ.ም ለ4ኛ ጊዜ ባሳተመውና “ምልከዓም ሰይፈ ነበልባል” የሚል ርዕስ በሰጠው መጽሐፉ፡፡ ምልክዓም ሰይፈ ነበልባል ከ”አልወለድም” እና “አንድ ለእናቱ” ቀጥሎ ብዙ አንባቢ ያገኘ መጽሐፍ መሆኑን አዲስ ዘመን ጋዜጣ በወቅቱ መዘገቡን አንብቤያለሁ፡፡ ምልክዓም ሰይፈ ነበልባል የመጽሐፉ ርዕስ ብቻ ሳይሆን ዋና ወኪል ባለታሪክም (ገፀ ባህርይ የሚባለው) ነው፡፡ አቤ፤ ሰዎች መብታቸውን ማስከበር ያለባቸው ከተወለዱና ካደጉ በኋላ ብቻ ሳይሆን ገና በእናታቸው ማህፀን ሳሉ…“እውነት በሌለበት ዓለም ለመኖር አልወለድም” ብለው እንዲሟገቱ የጻፈና በዚህም፤ መጽሐፉ ለእሳት፣ እሱ ደግሞ ለቁም እስር፣ ለግዞትና ለእንግልት የተዳረገ ጽኑዕ ደራሲ ነበር፡፡ “አልወለድም” የሚል ተዓምረኛ ፅንስ ፈጥሮ እንዳሳየን ሁሉ “ምልክዓም” የተባለ ሰው “ቤትኤሌፋኦስ” ብሎ በጠራት ሀገር ፈጥሮና በፕሮቴስታንት ሚሲዮን ስርዓት አሳድጐ ለጠቅላይ ሚኒስትርነት ማዕረግ ያበቃዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚመራትን አገር ህዝብ ሁሉ ስለሚወድና እንደቤተሰቡ ስለሚያምን በሚወዳቸው ሰዎች አማካይነት የተመረዘ ምግብ ይበላና ይሞታል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሊሞት ሲያጣጥር በኑዛዜ መልክ የተናገረውንና በህይወት እያለ “ለፓርላማ እያቀረበ ያስፀደቃቸው ናቸው” ብሎ ነው አቤ ዝርዝር ዕቅዶችንና የተደረጉ ክርክሮችን በዝርዝር ያሳየን፡፡ መጽሐፉ የሚጀምረው ከጠቅላይ ሚኒስትሩ የ”ውጭ ነፍስ፣ ግቢ ነፍስ” ጣር ላይ ነው፡፡ ከዚያም በህይወት ታሪክ መልክ መልእክቱን ያስተላልፍልናል። ምልክዓም ያገሩን ህዝብ በእጅጉ የሚወድና “ፈጣን ለውጥ” ማምጣት የሚፈልግ፣ በርካታ የለውጥ እርምጃዎችን ወስዶም በአገሩ ህዝብ ዘንድ ተወድዶ የሚከበር ጠቅላይ ሚኒስትር ነበር፡፡ “እኛ ከታላቅ ግብ የምንደርሰው በነፃነትና በኅብረት በምንሠራው ጠንካራ ሥራ ብቻ እንጂ የአንዳንድ መንግሥታት ጥሩንባዎች ሆነን በምናገኘው ምጽዋት አይደለም፡፡ እኛ ነፃ ሕዝብ ነን፡፡

የሚወዱንን የማንወድበት፣ የሚጫኑንን የማንቃወምበት ምክንያት የለንም” ይላል ምልክዓም የውጭ ፖሊሲውን አስመልክቶ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስም “ዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ዕርዳታና ብድር እንድንፈቅድላችሁ ዝለሉ ሊል ይችላል፡፡ ቶሎ ብለው “ስንት ጊዜ እንዝለል?” የሚል ጥያቄ የሚያቀርቡ መንግሥታት ይኖራሉ፡፡ አኛ ግን ቢያንስ “ለምን? ብለን እንጠይቃለን፡፡” ሲሉ አድምጠናቸዋል፡፡ ምልክዓም በሀገረ ቤትኤልፋኦስ ውስጥ “ፈጣን ለውጥ” ለማምጣት ሌት ከቀን ይሰራ ነበር፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም “ፈጣን ለውጥ” የሚሉትን ቃላት እንደ ዳዊት ከመደጋገም አልፈው በተግባር ለመተርጐም ደፋ ቀና ሲሉ ሞት ቀደማቸው፡፡ “ግማሾች ወገኖቼ በቁንጣን፤ ግማሾቹ በረሃብ ሲሞቱ ለማየት አልሻም፡፡ በሚገባ ሁኔታ ማደላደል፤ ቁንጣንንም ረሃብንም ማጥፋት ስለሚቻል ሁሉንም በሚገባ ለማደላደል ዝግጁ ነኝ” ይላል የአቤው ጠቅላይ ሚኒስትር ምልክዓም፡፡ በሶሻሊዝም ደቀመዝሙርነታቸው የሚታወቁት ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም፤ በአገሪቱ ውስጥ ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል እንዲኖር ተግተው እንደሚሰሩ፤ በተለይ አዲስ አበባን አሁን ካለችበት ሶስት ደረጃ ወደ ሁለት ለማጠጋጋት እንደሚጥሩ ሲገልጹ ነበር፡፡ ንግግራቸውን በተግባር ለመግለጥም የጋራ መኖሪያ ህንፃዎች በብዛት እንዲሰሩ ፓርቲያቸው ዕቅድ ነድፎ እየተንቀሳቀሰ ነበር፤ ነውም፡፡

የምልክዓምን ዋና ዋና ተግባራት በተመለከተ ደራሲው (አቤ ጉበኛ) እንዲህ ይገልፀዋል፡፡ “አምስት ዋና ዋና ግድቦች” አሰርቶ የኤሌክትሪክ ቢያዎች በብዛት እንዲቋቋሙና የመስኖ ልማት በጣም እንዲስፋፋ አደረገ፡፡ አርባ ታላላቅ ፋብሪካዎች፣ ስምንት መቶ ቀላል ኢንዱስትሪዎች፣ 550 ታላላቅ የማህበር እርሻዎች እንዲቋቋሙ አደረገ፤ ሁለት የብረት ማቅለጫ፣ አንድ የመዳብ ማቅለጫ ጣቢያዎችንም አቋቋመ፡፡ ከሶስት ቦታዎች ላይ የነዳጅ ዘይት ፍለጋ ሥራ እንዲጀመር አድርጐ ፍለጋው ታላቅ ተስፋ ባለው ሁኔታ ይጣደፍ ነበር” ኢህአዴግም ከዚህ በላይ የተጠቀሱትንና “ምልክዓም አከናወናቸው” የተባሉትን ተግባራት የመሰሉ የኃይል ማመንጫ፣ ፋብሪካ፣ የመስኖ ግድብና የነዳጅ ዘይት ፍለጋ ተግባራትን ትኩረት ሰጥቶ እያከናወነ ይገኛል፡፡ “ትምህርት ቤቶች በሁለት ዕጥፍ እንዲጨምሩ አደረገ፡፡ የሃገሩ አውራጃዎች በባቡር እንዲገናኙ ከማድረጉ በላይ በአንዳንድ ቀበሌዎችም የባቡር ሃዲድ መዘርጋት እንዲጀመር አስደርጓል” (ገፅ 27) በዘመነ ኢህአዴግም ትምህርት ቤቶች በእያንዳንዱ ቀበሌ ገበሬ ማህበር ከመሰራታቸው በተጨማሪ የዩኒቨርሲቲዎች ቁጥር ከሁለት ወደ ሰላሳ አንድ እንዲያሻቅብ አድርጓል፡፡ የባቡር መስመሩም እንደ አቤ ጉበኛው ምልክዓም ተጠናቅቆ ስራ ላይ ባናየውም ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት፤ እንዲያውም በአምስት ዓመቱ የለውጥና የተሃድሶ ዕቅድ ዘመን ውስጥ አምስት ሺህ ኪሎሜትር ሃዲድ ለመዘርጋት አቅዶ እየሰራ ነው፡፡ ግን ከሥራ ዘመኑ ላይ አቤ እና ኢህአዴግ የሚለዩበት መስመር አለ፡፡ የአቤው ምልክዓም ያንን ሁሉ ተግባር ያከናወነው በስልጣን ላይ በቆየባቸው 13 ዓመታት ሲሆን ኢህአዴግ ሊገነባ ያሰበው በአምስት ዓመታት ብቻ ነው፡፡

እርግጥ ኢህአዴግ 11 የሥልጣን ዘመናቱን የፈጀው በስብሰባና አገርን በማረጋጋት ላይ ነው (ከ1983-1994)፤ ከ1995 ዓ.ም በኋላ በተለይም ከ1997 ዓ.ምህረቱ የምርጫ ውጤት ጋር ተያይዞ ከእንቅልፉ ሊባንንና የሚታይ የልማት ውጤት ለማስመዝገብ ችሏል፡፡ “ህዝብ ወዶ ሲጠላኝ ከማየት አለመኖሬን እመርጣለሁ፡፡ …ተወዶ እንደመጠላት ተከብሮ በገዛ ተግባር እንደመናቅ ያለ የሞት ሞት ወዴት አለ” የሚለው ምልክዓም ፤ በራስ ጥረት ማደግ እንደሚቻል ጠንካራ እምነት ነበረው፡፡ መራሔ ኢህአዴጉ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስም፤ ዘላቂ ልማት የሚመጣው በሃገሬው ህዝብ ጠንካራ ጥረትና የተባበረ ትግል እንጂ በውጭ መንግሥታት ዕርዳታና ብድር አለመሆኑን ይናገሩ ነበር፡፡ ለማስረጃም ታላቁን የህዳሴ ግድብ በእኛው መዋጮና አቅም ለመገንባት መሠረቱን ጥለዋል፡፡ “አንድ አገር የተፈጥሮ ሃብቶቹን ለተወላጆቹ በበቂ ሊሰጥ ካልቻለ አገርነቱ ብቻ ሊያኮራ አይችልም። ለተራበና የዕለት ፍላጐቶቹን ካላገኘ ሰው ሀገርና ነፃነት ከሚለው ቃል ይልቅ ምግብና ልብስ የሚለው ቃል ይሰማዋል” ይላል ምልክዓም የሀገርን ትርጉምና የህዝብን ሀገራዊ ቁርኝት ሲገልጽ፡፡ ምልክዓም አስተዳደርን አስመልክቶም “ማንም ህዝብ ሥነ ሥርዓት ያለው አስተዳደር፣ ትክክለኛ ፍርድና ፀጥታ ያለው ኑሮ ከነፃነት ጋር ካላገኘ ምንም ነገር ሊሠራ አይችልም” የሚል አቋም ነበረው፡፡ ኢህአዴግም ምንም እንኳን ሃሳቡን በገቢር መግለጽ አቅቶት እየተንገዳገደ ቢገኝም “መልካም አስተዳደር የልማት መሠረት ነው” ብሎ እንደሚያምን ደጋግሞ ሲናገር ይደመጣል፡፡

እንዲያውም ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ጉቦኞችንና ለመልካም አስተዳደር ጠንቅ የሆኑትን ሰላቢዎች በሁለት በመክፈል “የመንግስትና የግል ሌቦች” ብለው መናገራቸው አይዘነጋም፡፡ ምልክዓም ዳቦንና ኑክሊዬርን በማነፃፀርም እንዲህ ብሎ ነበር “ያገራችን ህዝብ ሁሉ በቀላሉ ሊሠራቸው የሚችላቸውን ሥራዎች በተፋጠነና ጠቃሚ በሆነ መንገድ በመሥራት እንድንበለጽግ ነው፡፡ ከአቶሚክ ቦንብ ይልቅ ዳቦ ብዙ ፈላጊ አለው። ግዴላችሁም ሞኝ አንሁን፡፡ በዓለም ውስጥ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ሕዝቦች በረሃብ የሚሰቃዩት ምግብ ስላነሰ እንጂ የኒክሊዬር ቦምብ ስለጠፋ አይደለም” ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም የኢትዮጵያ ሕዝብ ቀንደኛ ጠላት ድህነት መሆኑን፣ ይህንን መሠረታዊ ጠላት ለማሸነፍም ከትጥቅ ትግሉ በላይ መራራ ትግል እንደሚጠይቅ ደጋግመው ይናገሩ ነበር፡፡ “የሀገራችንን ሕዝብ ሠርቶ እንዳይጠቀም እያሰናከልን ‘አገራችን ለውጭ አገር ዜጐች ክፍት ናት፡፡ እንግዳ ተቀባዮች ነን፡፡ ብዙ የውጭ አገር ዜጐች በሀገራችን ውስጥ በደስታ ይኖራሉ’ በሚሉ የራስ ማታለያ ቃሎች ራሳችንን እየሸንገልን በሀገራችን ያሉትን ጠቃሚ ጠቃሚ የሥራ ቦታዎች ለውጭ ዜጐች ብንሰጥ ሕዝቡ አውቆ ሊቃወመን ባይችል እንኳ እግዚአብሔር ይፈርድብናል” ይል ነበር ምልክዓም፡፡ ይህን ድርጊትም ኢህአዴግ እየፈፀመው ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም በየክልሉ ለውጭ ዜጐች ዓይናቸው ያየውንና ልባቸው የከጀለውን ያህል መሬት እየሰጠ፤ ዜጐቹን ግን “ደን ጨፍጭፈዋል” በሚል የዋህ ሰበብ ከደቡብ፣ ከኦሮሚያ እና ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በጠራራ ፀሐይ ሲያፈናቅልና ሲያባርር ተስተውሏል፡፡

አረብና ፓኪስታን መጥቶ በግሬደር ድራሽ አባቱን የሚያጠፋው ዛፍ ግን የኢትዮጵያ ሃብት አይደለም፡፡ ወይም ጥፋት የሚሆነው በኢትዮጵያውያን መጥረቢያ ሲቆረጥ ብቻ ነው፡፡ “አገራችንን ማልማት የሁላችንም ተግባር ስለሆነ ለዚህ ተግባር ከየግል ጥቅማችን በከፊል ለጥቂት ጊዜ መስዋዕት ማድረግ ግዳጃችን ነው፡፡ ብዙ ደሞዝ ያለን ከደሞዛችን እየቀነስን ለልማት ባጀታችን ማሙያ የገቢ ምንጭ መፍጠር አለብን፡፡ …40 ሚሊዮን የሆንን ያገራችን ሰዎች በዓመት አንዳንድ ብር ብናወጣ 40 ሚሊዮን ብር እናገኛለን፡፡ በዚህ በአንድ ዓመት በሚገኘው ብቻ ብዙ ክሊኒኮች፣ ብዙ ትምህርት ቤቶችና አንዳንድ መንገዶች መሥራት እንችላለን” (ገፅ 49፣ 50፣ 100-101) ኢህአዴግም ለሚያከናውነው የልማት ተግባር የአርሶ አደሩ ጉልበትና የከተማ ነዋሪው መዋጮ ከፍተኛ ዋጋ አላቸው ብሎ ያምናል፤ አምኖም ተግባራዊ እያደረገው ነው፡፡ የአቤ ጉበኛው ምልክዓም ስንፍናንም ይኮንን ነበር “የማይሠሩት የሚሠሩትን የሚንቁበትና የሚያጠቁበት ጊዜ አልፏል፡፡ ሠራተኞቻችን ትሁት የሆነ ንቃት መንቃት አለባቸው፡፡ ጨዋ የሆነ ደስታ መደሰትም ይገባቸዋል፡፡” (ገፅ 77) የሥራን ክቡርነት፣ የተመጻዳቂነትን መርዘኛነት ደርግ ገላልጦ ቢያሳይም ኢህአዴግ በተግባር አውሎታል፡፡ ዛሬ በየሰፈሩ ተደራጅተው ደረቅ ቆሻሻ የሚያነሱ፣ በጥርብ ድንጋይ ንጣፍ ህይወታቸውን የሚመሩ በርካታ ወጣቶችን ማየት የተለመደ ሆኗል።

ህዝቡ ቀልጣፋ አገልግሎት የሚያገኝበትን መንገድም ምልክዓም ተልሞ ነበር፡፡ “አንድ ባለጉዳይ ለማንኛውም የመንግሥት መ/ቤት ጉዳዩን ሲያመለክት በጠየቀበት ቀን መልስ ማግኘት አለበት” የሚሉና ሌሎች መሠረታዊ የአሠራር መመሪያዎችን ከማውጣቱም በላይ ለተግባራዊነቱ የቅጣት ህጐችንም አውጥቷል፡፡ ኢህአዴግም ምንም እንኳ በጽናት ባይቀጥልበትና የራሱን ሌቦች መቆጣጠር ባይችልም መሠረታዊ የአሠራር ለውጥ (ቢ.ፒ.አር) አካሂዶ በአንዳንድ መ/ቤቶች፣ ለምሳሌ ውልና ማስረጃና ኢሚግሬሽንና የዜግነት ጉዳይ ተቋማት የሚያስመሰግን ውጤት አሳይተው ነበር፡፡ ክትትል ባለመኖሩ ግን ወደነበሩበት ጐታታ አሠራር ተመልሰዋል፡፡ “…የግል ጠላቱን በመንግሥቱ ክብር ህግ ተጠግቶ የሚያጠቃ አገረ ገዥ፣ ዳኛ፣ ፖሊስ ወዮለት! ለሕዝብ አገልግሎት፤ ወንጀልን ለማስወገድና የሕዝብን መብትና ፀጥታ ለማስከበር ተመርጦ ራሱ የወንጀል መሪ የሆነ ባለሥልጣን ወዮለት” ሲል ምልክዓም ወስላታ ባለስልጣናቱን ያስጠነቅቅ ነበር፡፡ ኢህአዴግም ጠንከር ያለ እርምጃ መውሰድ አልቻለም እንጂ በጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካይነት “የእኛ ሌቦች” እያለ ባለሥልጣናቱን ሲወርፍ ይደመጥ ነበር፡፡ “ኪራይ ሰብሳቢ” የሚል የበረሃ ስምም አውጥቶላቸዋል፡፡ “የሰይጣን ሕግ ከእግዚአብሔር ሕግ ጋር ተስማምቶ ሰውን የሚጠቅም ሆኖ ባገኘው በርሱ ከመጠቀም አልመለስም” ይላል የአቤው ምልክዓም። ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም “ከበጣም መጥፎ መጥፎ፤ ይሻላል” የሚል ፈሊጥ ነበራቸው፡፡ “ሹመት የጡረታ አበል ወይም የማባበያ ጉቦ አይደለም” የሚል አቋም ያለው ምልክዓም “በመልካም አገር ተፈጥሮ መደህየት፣ የወንጀልና የሥራ ፈትነት ብዛት፤ የሰነፍ መሪዎችና ፈራጆች የሥራ ውጤቶች ናቸው” ይላል፡፡

እንደ ሃሳባቸው ስሉጥ የሥራ መሪዎችን (ባለሥልጣናትን) ማግኘት አልቻሉም እንጂ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስም አደገኛ ቦዘኔነትን ለማጥፋትና አምራች ኃይሉን ለማብዛት ጥረት ያደርጉ ነበር፡፡ በጣም የገረመኝ ጉዳይ ደግሞ የመኖሪያ ቤት ዕጥረትን ለማቃለል ምልክዓምም የተጠቀመበት ዘዴ ነው፡፡ “…1ኛ” የመንግስት ሠራተኞች ለግል ባለጥቅሞች ገባር በመሆን የኑሮ ቀንበር እንዳይከብዳቸው በማንኛውም መንገድ የኑሮአቸውን ሸክም ማቃለል አለብን፡፡ ሀ) የመንግሥት ሠራተኞች መኖሪያ ቤቶች መሥሪያ የ30 ሚሊዮን ብር በጀት ለመጀመሪያ ጊዜ መንግሥታችን መድቧል፡፡ ለ) በከተማዎቻችን ውስጥ ቤቶች እየተሰሩ ለመንግሥት ሠራተኞች ይሰጣሉ፡፡ የመንግሥት ሠራተኞችም ለቤቶቹ የሚወጣው ገንዘብ ከደሞዛቸው እየተቀነሰ እስኪመለስ ድረስ ይከፍላሉ። ሐ) ያከፋፈሉም ሁኔታ፤ ለግል ባለቤቶች መቶ ብር ኪራይ ይከፍል የነበረው ሐምሳ፤ ሐምሳ ይከፍል የነበረው ሃያ አምስት፤ በጠቅላላው ማንም ሰው ድሮ ይከፍል የነበረውን ግማሽ እየከፈለ መንግሥት ለሠራለት ቤት ያወጣውን ገንዘብ ይመልሳል፡፡ መ) ዕዳውን በረጅም ጊዜ ከፍሎ ከጨረሰ በኋላ ቤቱና ቦታው የራሱ ንብረት ሆኖ ይፀናለታል፡፡ 2ኛ. መንግሥት በአንድ በኩል ገንዘብ ሲያወጣ ባንድ በኩል ደግሞ ሠራተኞች ከሚኖሩባቸው ቤቶች የሚያገኘው ተመላሽ ገቢ ባጀቱን ሳያቋርጥ እንዲቀጥል ስለሚያደርግለት፤ ይህ ዓይነቱ ሥራ ሳያቋርጥ መቀጠል አለበት” (ገጽ 95-96) ኢህአዴግም የተጠቃሚውን ስብጥር አሰፋው እንጂ፤ በገቢር እየተረጐመው ያለው ይህንኑ የምልክዓምን ዕቅድ ነው ማለት ያስችላል፡፡ “እሱን አይደለም” ቢባል እንኳ “ተመሳሳይ ነው” ብሎ መከራከር ይቻል ይመስለኛል፡፡

ከ1997 ዓ.ም ጀምሮ በስፋት እየተገነቡ የሚገኙ የጋራ መኖሪያ ህንጻዎችና የ40/60 ፕሮጀክቶች ለዚህ አሳማኝ ዋቢዎች ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ የመሬት ባለቤትነትን በተመለከተም ምልክዓም የሚከተለውን አቅዶ ነበር “…የአንዳንድ ሰዎችን ቁጣ እየፈራን የሃገራችንን ጠቅላላ ጥቅም የሚጐዳ ነገርን ዝም ብለን ማየት የለብንም፡፡ 1ኛ) ለርሻ የሚሆኑ መሬቶች ሁሉ ለሀገራችን ገበሬዎች ይደለደላሉ፡፡ የጢሰኛና ገባር ታሪክም በዚህ ያበቃል፡፡ 2ኛ) በታወቀ ጊዜ በገንዘብ ሳይገዛ በልዩ ልዩ የማጭበርበር ምክንያት ብዙ የከተማ ቦታ የያዘ ከሁለት ቤቶች በላይ ያለው ሰው በቦዘን ያስቀመጠው ቦታ ቢገኝ፤ መንግሥት የቤት መሥሪያ ገንዘብ እያለው መሬት ለሌለው ሰው ይሰጣል፡፡ 3ኛ) ማንኛውም ሰው መንግሥት ሳያውቅ መሬት መግዛት፣ ሻጩም መሸጥ አይፈቀድለትም” (ገፅ 97) ሰው ከእንስሳት በታች ይታይ በነበረበት ዘመን ላይ አቤ ይህን ደፍሮ መጻፉ ያስደንቃል፡፡ ምንም እንኳ የጢሰኛና ገባርን ሥርዓት በማፈራረስ መሬትን ለአራሹ ያደረገው ደርግ ቢሆንም ኢህአዴግም ይህንኑ ሥርዓት ጠንክሮ ቀጥሎበታል፡፡ የህገወጦች የመሬት ወረራ ከቁጥጥሩ በላይ ስለሆነበትም ነባር ይዞታዎችን ሁሉ ወደ ሊዝ የሚያስገባ አዋጅ ለማውጣትም ተገዷል፡፡ “እኛ የሕዝብ ባለዕዳዎች ነን እንጂ ሕዝብ የኛ ባለዕዳ አይደለም፡፡ የተማርነውም የተሾምነውም በህዝብ ላይ ስለሆነ የሕዝብ አሸከርነታችንንና ባለዕዳ መሆናችንን ማመን አለብን” ይላል ምልክዓም፡፡ ኢህአዴግም መሠረታዊ የአሰራር ለውጥ (ቢ.ፒ.አር) እና የማህበራዊ አገልግሎት መልሶ ማዋቀር (ሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም) ለማምጣት ደፋ ቀና ሲል ነበር፡፡ ግን ሁሉም ተጨናግፎበታል፡፡

  • ከቤተክርስቲያን ጋር ፀብ የለንም፤ ለአመፃ አልመጣንም” (“የማህበረ ዘደቂቅ ኤሊያስ” መሪዎች)
  • “በማህራችን እኔ ኤልያስ ነኝ የሚል አላጋጠመኝም”
  • “ነብዩ ኤልያስ በነገረን መንገድ የጥንቷን ሃይማኖት እያስተካከልን ነው -
  • “ቅዱስ ኤልያስ በኢትዮጵያ ሚሊኒየም ወደ ምድር ወርዶ በእሳት ሰረገላ እየተዘዋወረ ነው”

ነብዩ ኤልያስ ለፍርድ ወደ ምድር ወርዶ በእሳት ሰረገላ እየታየ ነው ከሚለው እምነታቸው ጋር በተያያዘ ድንጋይ ተወርውሮባቸው በተፈጠረ ሁካታ ለሰባት ቀናት ታስረው የነበሩት አባ ዮሴፍ ብርሃነ፣ አርቲስት ጀማነሽ ሰለሞን፣ መምህር ወልደመስቀል ፍቅረማሪያም እንዲሁም ፕሮፌሰር ይስማማው አለሙ፤ ሃይማኖታችን ተዋህዶ ነው፤ ኦርቶዶክስ የሚለው ቃል አላግባብ የተጨመረ ነው ይላሉ፡፡ “ማህበረ ዘደቂቀ ኤልያስ” በሚል ስያሜ ራሳቸውን የሚጠሩት የማህበሩ መሪዎች፤ አዲስ ሃይማኖት እንዳልፈጠሩ ሲያስረዱ፣ የጥንቷን እውነተኛ ሃይማኖት ወደ ትክክለኛ ቦታዋ እንድትመለስ እያደረግን ነው ብለዋል፡፡ ይህን የምንሰራው ነብዩ ኤልያስ በነገረን መንገድ እንጂ እኛ በመሰለን መንገድ አይደለም የሚሉት የማህበሩ መሪዎች፤ በማህበሩ ውስጥ ኤልያስ ነኝ የሚል ሰው የለም ብለዋል፡፡

ከማህበሩ መሪዎች መካከል አንዱ የሆኑት አባ ዮሴፍ ብርሃነ “ኤልያስ ወደ ምድር መጥቷል” በሚለው እምነታቸው ዙሪያ ተጠይቀው፤ ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ አለምን ለመፋረድ ከገነት ወደ ምድር ወርዶ በእሳት ሰረገላ እየተዘዋወረ ነው ብለዋል፡፡ ኤልያስ መጥቷል ስላልን አይመጣም፡፡ እኛ ኤልያስ አልመጣም ስላልን አይቀርም ያሉት አባ ዮሴፍ፤ ኤልያስ እንደሚመጣ በመፅሃፍ ቅዱስ በግልፅ የተነገረ ስለሆነ ብቻ ሳይሆን የሚመጣበት ጊዜም ስለተጠቀሰ ጊዜውን አስልቶ ማወቅ ይቻላል ብለዋል፡፡ ከአንዳንድ ሰዎች ዘንድ ተቃውሞ እንደተሰነዘረባቸው ያመኑት አባ ዮሴፍ፤ እስካሁን ጉዳዩ በሲኖዶስ ቀርቦ እንዳልተወገዘና ሲኖዶሱ ጉዳዩን ቢመረምረው እንደሚወዱ ገልፀዋል። ማህበሩን ከተቀላቀለች አንድ አመት ከ7ወር እንደሆናት የገለፀችው አርቲስት ጀማነሽ፤ አንዳንድ ሰዎች ጀማነሽ የመሠረተችው አዲስ ሃይማኖት መጥቷል በሚል ህብረተሰቡን እያደናገሩ ነው ካለች በኋላ፣ እኔ የመሠረትኩት አዲስ ሃይማኖት የለም ብላለች፡፡ “ተዋህዶ” የሚለው ስም ከጥንት የኖረ የሃይማኖታችን መገለጫ እንጂ እኔ የፈጠርኩት አይደለም ያለችው አርቲስቷ፤ “እውነትን እየተናገረ በሚኖር ሰው ላይ ክፉ ስም እየለጠፉ ለማሳደድና እውነትን ለመደበቅ ከመሞከር እውነቱን መመርመር ይሻላል” ብላለች፡፡

ኦርቶዶክስ የሚለው ቃል አላግባብ የተጨመረ መሆኑን የሚያምኑት የማህበሩ መሪዎች፤ የጥንቷ እውነተኛ ሃይማኖት መገለጫዋ ተዋህዶ የሚለው ስያሜ ነው ብለዋል፡፡ “ኤልያስ መጥቷል ትላላችሁ፤ ኤልያስ በማህበራችሁ ውስጥ አለ ወይ?” በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ፤ “ኤልያስ መጥቷል አልመጣም የሚለው መልዕክት ሊያከራክር ቢችልም፣ እስካሁን በማህበራችን እኔ ኤልያስ ነኝ የሚል አላጋጠመኝም” ብላለች፡፡ መ/ር ወልደመስቀልም በበኩላቸው፤ በበረሃ ያሉ፤ በፆምና በፀሎት የተጉ አባቶቻችን ኤልያስ ተገልጦላቸዋል፣ ዳሷቸዋል፣ አነጋግሯቸዋል” ብለዋል፡፡ በፖሊስ የታሰሩበትን ምክንያት ተጠይቀው ሲመልሱ፣ በሚያዝያ 16 ቀን የኪዳነምህረትን ዝክር ለመዘከር 4 ኪሎ ቅድስት ስላሴ ቤተክርስቲያን አካባቢ ወደ ምትገኝ የማህበሩ መሰብሰቢያ ቤት ፀበል ፃዲቅ ይዘው በሚሄዱ አባላት ላይ አንዳንድ የሠፈሩ ወጣቶች ድንጋይ በመወርወራቸው በተፈጠረ አለመግባባት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ በወጣቶቹ ድርጊት አንዲት ታዳጊ መፈንከቷን የገለፁት የማህበሩ መሪዎች፤ በእለቱ በከሣሽነት ወደ ፖሊስ ጣቢያ ሄደው የከሳሽነት ፎርም ሞልተው ቃላቸውን ከሰጡ በኋላ፣ በጣቢያው አዛዥ ውሳኔ የከሳሽነት ቃላቸው ተቀይሮ በተከሳሽነት ቃላቸውን እንዲሰጡ መደረጋቸውን ተናግረዋል፡፡

ከከሳሽነት ወደተከሳሽነት እንዲቀየሩ የተደረገው ቀደም ሲል የአካባቢው ሰው ለፖሊስ ጣቢያው ተደጋጋሚ አቤቱታ በማቅረቡ መሆኑን መምህር ወልደመስቀል ተናግረዋል፡፡ ማህበሩ መርሃ ግብሮችን ሲያከናውን ድምጽ ይረብሸናል የሚሉ አቤቱታዎች እንደቀረቡብን ተረድተናል፣ ነገር ግን በፍርድ ቤት ሲቀርቡ በደፈናው ሁከት ፈጠራችሁ የሚል ክስ ነው የተመሰረተብን ብለዋል የማህበሩ መሪዎች፡፡ በመጀመሪያ የፍርድ ቤት ውሎ የዋስ መብታቸውን ቢጠይቁም፤ መርማሪው የአካባቢው ህብረተሰብ ቦታውን ለቀው እንዲወጡ የሚል አቤቱታ እያቀረበ ስለሆነ ጉዳዩ እስኪጣራ የዋስ መብታቸውን እቃወማለሁ በማለቱ ለ7 ቀናት በእስር መቆየታቸውን የገለፁት የማህበሩ መሪዎች፤ በመጨረሻ ግን ስትፈለጉ ትቀርባላችሁ ተብለው እያንዳንዳቸው በ500 ብር ዋስ እንደተለቀቁ ተናግረዋል፡፡

በአሜሪካ፣ “serial killer” ተብሎ በፖሊስ የሚታደን ሰው…

በኛ አገር “አርበኛ” ወይም “ጀግና” ተብሎ ሊወደስ ይችላል (በአብዮቱ አመታት ሲተላለቁ እንደነበሩት አብዮተኞች)

በፈረቃ ከምትሰራበት በርገር ኪንግ እንደወጣች ጠፍታ የቀረችው አማንዳ ቤሪ፣ “ፊቷን አየሁ፤ ድምጿን ሰማሁ” የሚል ሰው ሳይገኝ 11 አመታት አልፈዋል። የጠፉ ልጆችና ልጃገረዶች፣ በሁለት ቀናት ውስጥ ተፈልገው ካልተገኙ ብዙውን ጊዜ መጨረሻቸው አሳዛኝ ነው። ተገድለው ነው የሚገኙት። ሳምንት ሙሉ ተፈልጋ ያልተገኘችው አማንዳ፣ ከዚህ ዘግናኝ ህልፈት አትተርፍም የሚል ነበር የመርማሪዎች ግምት። አስገራሚው ነገር ከሳምንት በኋላ፣ ለእናቷ አንድ የስልክ ጥሪ ደረሰ። የተደወለው ከአማንዳ ሞባይል ነው። የእናቷን ድንጋጤና ጭንቀት ልክ አልነበረውም። ስልኩን ሲያነሱት ግን፣ የልጃቸውን ድምፅ አልሰሙም። ሞታለች የሚል መርዶም አይደለም። ከአማንዳ ጋር ተጋብተን ሚስቴ ሆናለች የሚል የወንድ ድምፅ ነው የሰሙት። በኢትዮጵያዊኛ ቋንቋ ብንተረጉመው፣ “ጠልፌ ወስጃታለሁ፤ ጠልፌ አግብቻታለሁ” እንደማለት ነው። በቃ፣ ስልኩ ተዘጋ።

የአማንዳ እናት መረጃውን ለፖሊስ ቢያደርሱም፣ የፖሊስ ምርመራና ፍለጋ ባይቋረጥም፣ ውጤት አልተገኘም። ከአመት በፊትም፣ ከዚያው አካባቢ አንዲት ወጣት ሴት ጠፍታለች። ከአማንዳ በኋላም እንዲሁ፣ ከተመሳሳይ ቦታ ሌላ የ14 አመት ሴት እንደወጣች ቀርታለች። የት ይግቡ፣ የት ይድረሱ ፍንጭ አልተገኘም። በእርግጥ አንዲት ጠንቋይ በቴሌቪዥን ስርጭት አማንዳ ህይወቷ አልፎ አስከሬኗ ጥልቅ ባህር ውስጥ ሰጥሟል ብላ እንደተናገረችውም አልሆነም። ሶስቱ ሴቶች ከነሕይወታቸው ከአስር አመት በላይ ሲሰቃዩ የኖሩት፣ አማንዳ ከጠፋችበት አካባቢ ብዙም የማይርቅ መኖሪያ ቤት ውስጥ ነው - በሶስት በአራት ኪሎሜትር ርቀት። በኤርየል ካስትሮ ተጠልፈው ከታገቱበት እለት ጀምሮ፣ ሶስቱ ሴቶች ከቀን ቀን፣ ከአመት አመት፣ ቤት እንደተዘጋባቸው መከራ ይበላሉ።

ለመውጣት ቢሞክሩ፣ ድብደባውና እርግጫው! አሁንም በኢትዮጵያዊኛ ቋንቋ እንግለፀው ከተባለ፣ “ከቤት ንቅንቅ ብትይ እግርሽን እሰብረዋለሁ” እያለ ሚስቱን ነጋ ጠባ የሚያሰቃይ ባል እንደማለት ነው። እንዴት ብትሉ፤ ከሁለት ሳምንት በፊት ኢቲቪ በሁለት ክፍል ካቀረበው ድራማ መልሱን ማግኘት ይቻላል። “ጠልፎ ማግባት” በህግ የተከለከለ የወንጀል ድርጊት መሆኑን ለማሳየትና፣ “ለህብረተሰቡ ግንዛቤ ለማስጨበጥ” ታስቦ የተሰራ ድራማ ነው። እንግዲህ አስቡት። “ጠልፎ ማግባት” ብዙም እንደ ወንጀል ስለማይቆጠር፣ “በሽማግሌና በእርቅ” ሊያልቅ የሚችል ቀላል ጉዳይ እንደሆነ ተደርጎ ስለሚታሰብ… ያን ያህልም “ጉድ! ጉድ! አቤት ጭካኔ!” የሚያሰኝ አይደለም ማለት ነው። እናም፤ “ጠለፋ ወንጀል ነው” እያሉ “በድራማ ግንዛቤ ለማስጨበጥ ጥረት ማድረግ” አስፈለገ። ገና እዚህ ደረጃ ላይ ነን ያለነው። ከኢትዮጵያውያን መካከል ግማሾቹ፣ ባል ሚስቱን የመደብደብ መብት አለው ብለው እንደሚያምኑም ባለፉት አስር አመታት የተካሄዱ ሶስት ተከታታይ ጥናቶች ያረጋግጣሉ።

በአጭሩ፣ ጠልፎ ማግባትና ማሰቃየት፣ ብዙ ጣጣ የለውም። ድብቅነትን አይጠይቅም። በአሜሪካ ግን፣ ጣጣው ብዙ ነው። ጠልፎ ማግባት ይቅርና፣ ሚስትን “የት ወጣሽ የት ገባሽ” እያሉ ማሰቃየት እንደ ተራ ነገር አይቆጠርም። በዝምታ የሚታለፍ ቢሆን ኖሮማ፣ ኤርየል ካስትሮ ከመጀመሪያ ሚስቱ ጋር ባልተለያየ ነበር። የኤርየል ቤትና የሚስቱ ወላጆች ቤት ቅርብ ለቅርብ ቢሆንም፣ እየመጡ እንዲጠይቋት ወይም እየሄደች እንድትጠይቃቸው አይፈልግም ነበር። አንዳንዴ እሱ በማይኖርበት ሰዓት እህቷ ልትጠይቃት ስትመጣ እንኳ፣ በሩ ስለሚቆለፍ መግባት አትችልም። ኤርየል፣ ሚስቱን ቤት ውስጥ ቆልፎባት ነው የሚሄደው። ከዚያም ድብደባ ተጨመረበት። አንዴ አፍንጫዋን ሰብሯታል። ሚስቱን በመደብደቡ ሁለቴ የታሰረው ኤርየል፣ ባህሪውን ሊያሻሽል ስላልቻለ ሚስት በፍቺ ጥላው ወጣች - በፖሊስ ታጅባ። “ሚስቱን ቢደበድብ መብቱ ነው” የሚል አይነት አስተሳሰብ በስፋት የሌለበት አገር ውስጥ፣ “ውልፊት ትይና እግርሽን እሰባብረዋለሁ” እያለ እድሜ ልክ ሚስቱን እያሰቃየ መኖር አይቻልም - ማንም እንዳያውቅ ደብቆ ካላሰቃየ በቀር። ኤርየልም፣ ይህንኑን ነው ያደረገው - ጠልፎ እየወሰደ በድብቅ ማሰቃየት።

እንደ ኢትዮጵያ በመሳሰሉ አገራት፣ በሃይማኖትና በብሄረሰብ ስም፣ በአገርና በህዝብ ስም፣ ሰውን የማጥቃትና የማሰር፣ የማሰቃየትና የመግደል… ቅስቀሳዎች ወይም ዘመቻዎች በየጊዜው በግላጭ ይፈፀሙ የለ? ይህንን የሚፈፅሙ ክፉ ሰዎች፣ ለጭካኔያቸው ሰበብና ማመካኛ አያጡም። እንዲያውም፣ “አገር ወዳድ አርበኛ፣ ቆራጥ አብዮተኛ፣ የቁርጥ ቀን ጀግና”… የሚል ውዳሴ ይጎርፍላቸዋል። ስቃይና ግድያ የሚፈፅሙትም በግላጭ ነው። እንደ አሜሪካ በመሳሰሉ በስልጣኔ ደህና የተራመዱ አገራት ውስጥ ግን፣ ሰውን በግላጭ ለማሰቃየትና ለመግደል የሚያስችል ሰበብና ማመካኛ ማግኘት ከባድ ነው። ክፉ ሰዎች፣ በግላጭ እንዳሻቸው ጭካኔ እየፈፀሙ በየአደባባዩ መፈንጨት አይችሉም። በድብቅ ስቃይና ግድያ ለመፈፀም የሚሞክሩ ግን አይጠፉም - ለምሳሌ ልማደኛ ነፍሰ ገዳዮች (serial killers)። ልዩነቱን አያችሁት። በኋላ ቀር አገራት ውስጥ፣ ክፉ ሰዎች ለጭካኔያቸው ብዙ አይነት ማመካኛ ማቅረብ ስለሚችሉ፣ በአደባባይ ሰውን እያሰቃዩና እየገደሉም፣ እንደ ጀግና ወይም እንደ አርበኛ ይታያሉ። በስልጣኔ ደህና የተራመዱ አገራት ውስጥ ግን፣ ክፉ ሰዎች “ልማደኛ ነፍሰ ገዳይነታቸውን” የሚሸፋፍኑበት እድል ስለሌላቸው በፖሊስ ይታደናሉ። እንደ ኢትዮጵያ በመሳሰሉ አገራት፣ “ልማደኛ ነፍሰ ገዳዮች (serial killers) የሌሉ ይመስለናል። በሌላ ስም ስለምንጠራቸው ነው - አርበኛ፣ አብዮተኛ፣ ጀግና እየተባሉ ይጠራሉ። እንደ ኤርየል ካስትሮ፣ በድብቅ የእገታና የማሰቃየት ጭካኔ የሚፈፅሙ ሰዎች በአገራችንና በሌሎች ኋላቀር አገራት የሌሉ ከመሰለ ንም ተሞኝተናል። ሞልተዋል። ግን፣ ጭካኔያቸውን ያን ያህልም መደበቅ አያስፈልጋቸውም። ሳልፈቅድልሽ ከቤት ወጥተሻል ብሎ ሚስቱን ቢደበድብ ብዙም ችግር አይገጥመውማ።

ባለ 5 ኮከቡ ካፒታል ሆቴልና ስፓ ትናንት ተመርቆ አገልግሎት ጀመረ፡፡ በ172 ሚሊየን ብር የተሠራው ሆቴሉ 114 የመኝታ ክፍሎች አሉት፡፡ በአቶ የማነ ገ/ሥላሴ ባለቤትነት የተገነባው ይኼ የግል ሆቴል መዋኛ፣ የሴቶችና የወንዶች መታሻ ክፍሎችና መዋቢያ፣ አንድ ፎቅ ጂምናዚየም፣ ባር፣ ላውንጅ፣ የስብሰባ አዳራሾች አሉት፡፡ ግንባታው አምስት ዓመት የፈጀው ሆቴል፤ በማስፋፊያው ባለ 11 ፎቅ ሕንፃ እያስገነባ ሲሆን ከምድር በታች ሁለት ፎቅ የመኪና ማቆሚያ አለው፡፡

ሆቴሉ በአሁኑ ወቅት ለ225 ዜጐች የሥራ ዕድል የፈጠረ ሲሆን የሠራተኞቹን ቁጥር 270 የማድረስ ዕቅድ አለው፡፡ አቶ የማነ ገ/ሥላሴ የሆሲ ትሬዲንግ ሃውስ ባለቤት ሲሆኑ ድርጅታቸው አሉ ከሚባሉት የገቢና ወጪ ንግድ ድርጅቶች አንዱ ነው፡፡ ሆሲ በብረታ ብረት ማሽኖች፣ መሳሪያዎችና ሌሎች ተዛማጅ ንግዶች ላይ የተሰማራ ሲሆን፤ የእርሻ ምርት ውጤቶችንም ለውጭ ገበያዎች በማቅረብ ይታወቃል፡፡

የማተሚያ ማሽኑ ዋጋ 8ሺ ዶላር ነው፤ ስምንት ሺ ሽጉጦችን ሊሰሩበት ይችላሉ። ፅሁፍ የሚያትም ሳይሆን ሽጉጥ ወይም ሌላ እቃ የሚያትም ማሽን ነው - 3D printer ይሉታል። የዘንድሮ ምርጥ ፈጠራ እንደሆነ የተነገረለት “ቅርፅ አታሚ ማሽን”፣ በሚቀጥሉት አመታት ገበያውን እንደሚያጥለቀልቅ ተተንብዮለታል። ትንቢቱ ወር ሳይሞላው፤ አለምን ሲያነጋግር የሰነበተ የህትመት ውጤት ብቅ አለ - በማተሚያ ማሽን የተሰራ የመጀመሪያው ሽጉጥ። መልኩ ከዘመናዊ የቢሮ ፅሁፍ ማተሚያ ማሽን በመልክ ብዙም አይራራቅም። አሰራሩም ተመሳሳይ ነው - ከኮምፒዩተር በሚደርሰው ትዕዛዝ አትሞ ማውጣት (ፅሁፍ ሳይሆን ቅርፅ)። የመጀመሪያው የሽጉጥ እትም በዚሁ ሳምንት በአደባባይ ተሞክሮ የመጀመሪያውን ጥይት ተኩሷል። ዲፈንስ ዲስትሪቢዩተር በተባለ ኩባንያ ተሰርቶ የተሞከረው ሽጉጥ Liberator የሚል ስም ተሰጥቶታል - ነፃ አውጪ እንደማለት። ሽጉጡ ከፕላስቲክ የተሰራ ቢሆንም፣ ማንም አላናናቀውም - የመተኮስ ስራውን በአግባቡ የሚያውቅ ነውና። ፍርሃት ያደረባቸው ግን አሉ።

ብዙዎቹ የመፈተሻ መሳሪያዎች፣ ብረታማ ነገሮችን ለይተው እንዲያሳዩ የተሰሩ ናቸው። የፕላስቲክ ሽጉጥ የታጠቀ ሰው፣ የፍተሻ መሳሪያዎች ሳያግዱት ማለፍ የሚችል መሆኑ፣ አንዳንድ የአሜሪካ ህግ አውጪ ምክርቤት አባላትን አሳስቧል። የጦር መሳሪያ ቁጥጥር አከራካሪ በሆነበት ወቅት፣ የብዙዎችን ትኩረት የሳበ አዲስ አይነት ሽጉጥ መፈጠሩ፣ አጋጣሚውን አስገራሚ አድርጎታል። ደግሞም ማንም ሰው በየቤቱ ኮምፒዩተርና “ፕሪንተር”ን እየተጠቀመ ሊፈበርከው ይችላል። በእርግጥ “ማንም ሰው ይችላል” የሚለው አነጋገር የተጋነነ ነው። ከኮምፒዩተሩ ወደ ፕሪንተሩ የሚተላለፈውን ትዕዛዝ (ንድፍ) አስተካክሎና ጠንቅቆ ማወቅ ያስፈልጋል። ይህንን ደግሞ “ማንም ሰው ይችለዋል” የሚባል አይደለም። ነገር ግን፤ ብዙዎችን አላስጨነቃቸውም።

ምክንያቱም፣ የአዲሱ ሽጉጥ ንድፍ በኢንተርኔት ተሰራጭቷል። ፎርብስ መፅሄት እንደዘገበውም በጥቂት ቀናት ውስጥ ከ100 ሺ በላይ ሰዎች፣ ንድፉን ከኢንተርኔት አግኝተው የራሳቸው አድርገውታል። ደግሞም፣ ሌሎች አማራጮች አሉ። የጦር መሳሪያ ባለቤት የመሆን መብት እንዲከበር በሕገመንግስት ባወጀችው አገር ውስጥ፣ መንግስት በጦር መሳሪያ ላይ አዳዲስ የቁጥጥርና የገደብ ህጎችን ማዘጋጀቱ ያስቆጣቸው ሰዎች ብዙ አማራጮችን እየፈጠሩ ነው - ለምሳሌ፣ አንድ የዩኒቨርስቲ ተማሪ፣ የሽጉጥ ንድፍ ሰርቶ በኢንተርኔት አሰራጭቷል። ይሄኛው ሽጉጥ 400 ጥይቶችን በመተኮስ በተግባር የተሞከረ ሲሆን፣ ከ400 ሺ በላይ ሰዎች የሽጉጡን ንድፍ ከኢንተርኔት ወስደዋል። የአሜሪካ ነገር፣ አጃኢብ ነው።

አውሮፕላኖች በሚንደረደሩበት አውላላ ሜዳና ከፍተኛ ጥበቃ በሚደረግበት ኤርፖርት፣ የጥይት ድምፅ ሳይሰማ የተዘረፈው የ50 ሚሊዮን ዶላር አልማዝ፣ ከሶስት ወር የፖሊስ ክትትል በኋላ፣ ሰሞኑን ዱካው ተገኘ። ዝርፊያውን የፈፀሙ ስምንት ሰዎችን ከነተባባሪዎቻቸው ለመያዝና የተዘረፈውን አልማዝ ለማስመለስ በርካታ የአውሮፓ አገራትን ያዳረሰ ክትትል ሲያካሂዱ የከረሙ መርማሪዎች፣ በጣሊያን፣ በቤልጄምና በቱርክ ውጤት ቀንቷቸዋል። የካቲት 10 ቀን ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ነው በቤልጄም ዋና ከተማ ከሚገኘው የብራስልስ ኤርፖርት አልማዙ የተዘረፈው። ከኤርፖርቱ አጠገብ፣ ጅምር የህንፃ ግንባታ ውስጥ ተደብቀው ያመሹት ስምንቱ ዘራፊዎች፤ የኤርፖርቱን አጥር ሲተረትሩ ማንም እንዳያያቸው ተጠንቅቀዋል። ወደ ውስጥ ከገቡ በኋላ ግን፣ በድብቅ ለመሽሎክሎክ አልሞከሩም። በተተረተረው አጥር ሁለት ጥቋቁር መኪኖችን እያሽከረከሩ ወደ አውሮፕላን መንደርደሪያው አመሩ።

ስምንቱ ዘራፊዎች እንደ ፖሊስ ለብሰው መሳሪያ ታጥቀዋል። በእርግጥ መሳሪያቸው የቤልጄም ፖሊሶች የሚጠቀሙበት አይነት ሳይሆን ክላሺንኮቭ ነው። ግን ከርቀት ይህንን ለይቶ የሚያስተውል አይኖርም። የፖሊስ ታርጋ የተለጠፈባቸው ሁለቱ ጥቋቁር መኪኖች፣ ኮፈናቸው ላይ ሰማያዊ የፖሊስ መብራቶች ተተልክሎላቸዋል። ማንም አላስቆማቸውም። በቀጥታ የአውሮፕላን መንደርደሪያዎችን እያቆራረጡ፣ ወደ ስዊዘርላንድ ለመብረር የተዘጋጀች መካከለኛ አውሮፕላን ጋ ደረሱ። ሌላ መኪና ለትንሽ ቀድሟቸዋል። ከእቅዳቸው ዝንፍ ያለ ነገር የለም። ከነሱ ቀድሞ የደረሰው መኪና፣ እንደ ካዝና በጠነከሩ ብረቶች የተሰራ የውድ እቃዎች ማመላለሻ ነው - ውድ የአልማዝ ጠጠሮችን ወደ አውሮፕላኑ የሚያደርስ። የመኪናው በር ተከፍቶ፣ እፍኝ እፍኝ የማይሞሉ 130 የአልማዝ ከረጢቶች ወደ አውሮፕላኑ ለማስገባት… ከዚያም አውሮፕላኑ ተነስቶ ለመብረር፣ ከ15 ደቂቃ በላይ መዘግየት እንደሌለበት ትዕዛዝ ተሰጥቷቸዋል። ዘራፊዎቹ ትክክለኛ መረጃ ባይኖራቸው ኖሮ፣ በትክክለኛው ሰዓት ባልደረሱ ነበር።

የአልማዝ ከረጢቶቹ ወደ አውሮፕላኑ ከገቡ በኋላ ለበረራ ሊነሳ ሲል ሁለት መኪኖች ከተፍ አሉ። የፖሊስ የደንብ ልብስ አድርገው፣ ፊታቸውን በጭንብል ሸፍነው፣ መሳሪያቸውን ወድረው ወደ አውሮፕላኑ የተንደረደሩት ዘራፊዎች፣ ፓይለቱንና የጥበቃ ሰራተኞችን በማስፈራራት የወርቅ ከረጢቶቹን ለመውሰድ ጊዜ አልፈጀባቸውም። በ20 ደቂቃ ውስጥ 50 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጡ የአልማዝ እንቁዎችን ይዘው እንደአመጣጣቸው ተፈተለኩ - ግርግር ሳይፈጠር፣ የጥይት ድምፅ ብቻ ሳይሆን የሃይለ ቃል ድምፅ ሳይሰማ ዘረፋው ከመጠናቀቁ የተነሳ፤ ተሳፋሪዎቹ ምን እንደተፈጠረ አላወቁም። በረራው እንደተሰረዘና ዘረፋ እንደተፈፀመ ሲነገራቸው ማመን አልቻሉም ነበር። ስምንቱን ዘራፊዎች ከነተባባሪዎቻቸው ለመያዝ በበርካታ የአውሮፓ አገራት ለሶስት ወራት ሲካሄድ የቆየው የፖሊስ አደን፣ በዚህ ሳምንት በከፊል ውጤታማ ሆኗል።

ከዘራፊዎቹ መካከል አንዱ በጣሊያን ከ8 ተጠርጣሪ ተባባሪዎች ጋር የተያዘ ሲሆን፤ በስዊዘርላንድ ሌሎች ተባባሪዎች በቁጥጥር ስር ሲውሉ የተወሰነው ያህል አልማዝም ተገኝቷል። በቤልጄም ደግሞ ከሃያ በላይ ሰዎች ታስረዋል። በኤርፖርቱ የተፈፀመው ዝርፍያ፣ በታሪክ ከተመዘገቡ ትልልቅ የአልማዝ ዝርፊያዎች መካከል በሁለተኛ ደረጃነት የሚጠቀስ ቢሆንም፤ አልማዝን ማጓጓዝ ግን ለቤልጄም ኤርፖርቶች የእለት ተእለት ስራ ነው። በአለማችን ለገበያ ከሚቀርቡ የአልማዝ ጌጣጌጦች መካከል ግማሽ ያህሉ ቤልጄምን ሳይረግጥ አያልፍም - የአልማዝ ማዕድን ተሞርዶና ተጣርቶ አምሮበት የሚወጣው ቤልጄም ውስጥ በሚገኙ ኩባንያዎችና ባለሙያዎች ነው። በየእለቱ፣ ቤልጄም በአማካይ የ200 ሚሊዮን ዶላር አልማዝ ታስተናግዳለች።

ከካህሊል ጂብራን አጫጭር ተረቶች አንዱ እንደሚከተለው ይላል፡- አራት ባሪያዎች አንዲትን ያረጀች ንግሥት በተኛችበት ያራግቡላታል፡፡ ንግሥቲቱ የተኛችው ዙፋኗ ላይ ነው፡፡ ታንኮራፋለች፡፡ እጭኗ ላይ አንዲት ድመት ወደ ባሪያዎቹ በዳተኛ አስተያየት እያየች ባሪያዎቹ ለሚነጋገሩት ምላሽ ትሰጣለች - በድመትኛ! አንደኛው ባሪያ “ይህቺ አሮጊት እንቅልፍ ሲወስዳት መልኳ እንዴት ያስጠላል፡፡ ለምቦጯ እንዴት ተንጠልጥሏል፡፡ ደሞ ኩርፊቷ ዲያብሎስ ሠርንቆ የያዛት እኮ ነው የሚመስለው” አለ ይሄኔ እመት ድመት ሚያው ሚያው አለች፤ በድመትኛ፡፡ ትርጉሙም - “ከአንተ ካልተኛኸውና ነቅተህ ባሪያ ሆነህ ከምታስጠላው የበለጠ አስታጠላም አለችው፡፡ ሁለተኛ ባሪያ “እንቅልፍ፤ የተጨማደደ ቆዳዋን የሚያቃናላት መሰላት እንዴ? የባሰኮ ነው የሚያጨማድዳት! የሆነ የተንኮል ነገር ነው መቼም እያለመች ያለችው” ይሄኔ እመት ድመት ሚያው ሚያው አለች በድመትኛ፡፡

ትርጉሙም - “እስቲ አንተም ተኛና ስለነፃነትህ አልም” ሶስተኛው ባሪያ ደሞ ተናገረ - “ምናልባት እስከዛሬ ያረደቻቸውን ሰዎች የቀብር ስርዓት እያየች ይሆናል” እመት ድመት በድመትኛ ቋንቋ ሚያው ሚያው አለች፡፡ “አሄሄ! እሷማ የምታየው የአያት ቅድመ አያትህንና የልጅ ልጆችህን ቀብር ነው!” አራተኛው ባሪያ እንዲህ አለ - “ስለ እሷ መናገራችን ጥሩ ነው፡፡ እዚህ ተገትሮ ለእሷ ማራገብ ግን በጣም ይደክማል” እመት ድመት በሚያው ሚያውኛ መለሰች፡፡ “ገና ዕድሜ-ልክ ታራግባለህ፤” ደሞም በመሬት የሆነው በመንግሥተ ሰማይም ይደገማል” ልክ ይሄን እያወሩ ሳሉ አሮጊቷ ንግሥት የሰማች ይመስል፤ በእንቅልፍ ልቧ እራሷን በአዎንታ ነቀነቀች፡፡ ዘውዷም ከጭንቅላቷ ተንሸራቶ መሬት ላይ ወደቀ፡፡ ከባሪያዎቹ አንዱም፤ “ኧረ! ይሄኮ መጥፎ ምልኪ ነው” አለና ሟርቱን አሰበ፡፡ እሜት ድመትም በሚያው ሚያውኛ “ያንዱ መጥፎ ምልኪ ለሌላው በጐ ምልኪ ነው” አለች፡፡

ሁለተኛው ባሪያም፤ “አሁን ብትነቃና ዘውዱዋ መውደቁን ብታይስ ጐበዝ! ሁላችንን ታርደናለች” እመት ድመት በሚያው-ሚያውኛ - “ከተወለዳችሁ ከመጀመሪያ ቀን ጀምሮ ስታርዳችሁ ነው የኖረችው፡፡ ችግሩ፤ አይታወቃችሁም” ሦስተኛው ባሪያም እንዲህ አለ “አዎን ታርደናለች፡፡ ስሙንም ለአማልክት የሚከፈል መዋስዕትነት ትለዋለች” እመት ድመትም በሚያው ሚያውኛ “ደካሞች ብቻ ናቸው የአማልክት መስዋዕት የሚሆኑት” አለች፡፡ አራተኛው ባሪያ ሌሎቹን አፋቸውን አዘግቶ በእንክብካቤ ዘውዱን አንስቶ፤ አሮጊቷ ንግሥት እንዳትነቃ አድርጎ መልሶ ጫነላት፡፡ እመት ድመትም በድመትኛ ተናገረች፡- “እንዴ የወደቀን ዘውድ መልሶ የሚያነሳ ባሪያ ብቻ ነው” አለች፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ንግሥቲቱ ነቃች፡፡ አካባቢዋን አየች፡፡ አዛጋችና፤ “በህልሜ አንድ ዋርካ ሥር አራት አንበጦችን አንዲት ጊንጥ ስታባርራቸው አየሁ፡፡ ጥሩ ነገር አይመስለኝ ህልሜ” አለች፡፡ ይሄን ብለ መልሳ አንቀላፋች፡፡ ማንኮራፋቷንም ቀጠለች፡፡ አራቱ ባሪያዎችም ማራገባቸውን ቀጠሉ፡፡ ድመቷም በሚያው-ሚያውኛ ቋንቋ፤ “ቀጥሉ፡፡ ማራገባችሁን ቀጥሉ፡፡ምድረ-ደደብ ሁሉ ቀጥሉ!! የምታራግቡት እናንተኑ የሚበላችሁን እሳት ነው፡፡ ቀጥሉ!!”

                                                            * * *

ካልተኛኽ ግን ባሪያ ሆነህ የቀረኸው፣ የተኛ ይሻላል፤ ከመባል ይጠብቀን፡፡ አንድ ግፍ አያት-ቅድመ አያታችንን ያጠፋው ሳያንስ፤ ለልጅ ልጆቻችን ከተረፈ ከእርግማን ሁሉ የከፋ እርግማን ነው! የማራገብ አደጋ ለሀገርና ለህዝብ የማይበጅ ፅኑ ጠላት ነው፡፡ በቀላሉ ተዋግተን ልናጠፋው ከቶ አንችልም! በተለይም ደግሞ የምናራግበው እኛኑ መልሶ የሚፈጀንን ከሆነ አሳሳቢ ነገር ይሆናል፡፡ የተውነውን፣ የጣልነውን፣ አንዴ የተላቀቅነውን አስተሳሰብ መልሰን ለማንሳት ከመሞከር ያድነን፡፡ የአሸነፍነውንና የተገላገልነውን አስተሳሰብ መልሰን ለማስተናገድ ዝግጁ አለመሆን ብልህነት ነው፡፡ ከዘመነ-መሣፍንት እስከ ነጋሲው አገዛዝ ድረስ፣ አልፎም ከወታደራዊው ሶሻሊዝ ወዲህም እስከ ብሔር-ብሔረሰባዊ ዲሞክራሲ ድረስ ረዥም መንገድ ሄደን፤ ሕግና ሥርዓት ልናስከብር፤ የሻይ ቤት የኬክ ቤት አገር ሳይሆን ትልቅ ኢንዱስትሪ ልንገነባ፤ በምንም ዓይነት ሰው ለሰው የማይበዘበዝባት፣ ዲሞክራሲያዊ አስተዳደር የሚሰፍንባት፣ እኩልነት ያረበበባት፣ ዘረፋና ውንብድና የማይታይባት፣ ሉዐላዊነቷ የተከበረ ቆንጅዬ አገር ልንመሰርት፤ ቃል ከገባን ውለን አደርን፡፡

በረዥሙ መንገድ ላይ አንዳንዶቹ ተሳክተው “እሰይ አበጀህ የእኛ ሎጋ” ሲያሰኙን፣ ሌሎቹ ከሽፈው ምነው ባልነካካናቸው ኖሮ አሰኝተው አንገታችንን ሲያስቀረቅሩን፤ የውሾን ነገር ያነሳ ውሾ ይሁን ሲያስብሉን እዚህ ደርሰናል፡፡ አሁንም ቢሆን “አለባብሰው ቢያርሱ በአረም ይመለሱ” ነውና፤ ዐይናችን እያየ የተፋጠጡንን የሙስናና የመልካም አስተዳደር አደጋዎች እንዲሁም የሚሥጥራዊነት አባዜ (ከግልፅነት አንፃራዊ በሆነ አቋም - as opposed to እንዲሉ) ካልተዋጋንና ወደ ግልፅ ውንብድና ሊሸጋገር አንድ አሙስ የቀረውን የሥርዓት-አልባነት፣ የሌብነትና የጭለማ-ሽምቅ ዘረፋ (ለአፍሪካ ህብረት 50ኛ ዓመት በዓል ሰሞን ብቻ ሳይሆን ለዘለቄታውም ልንፋለመው ብንፈጠም መልካም ነው፡፡

ገንዘብ እንዴት ልሰብስብ እያልን ገንዘብ ሲዘረፍ አላየሁም ማለት መቼም አያዋጣንም፡፡ እስከ ናይጄሪያና ኬንያ ዘረፋ ድረስ የከፋ ደረጃ አልደረስንም ብለን መፅናናት አንችልም፡፡ ጥፋት እያባረረን ነው፡፡ ጥፋቱ እስካለ ድረስ ሸሸን ማለት ከንቱ ነው፡፡ ለዚህ ነው “አሳዳጅ ካልተወ የሸሸ መች አመለጠ” የሚባለው፡፡ “…ትቻቸዋለሁ ይተውኝ አልነካቸውም አይንኩኝ ብለህ ተገልለህ ርቀህ ዕውነት ይተውኛል ብለህ እንዴት ተስፋ ታደርጋለህ? የተወጋ በቅቶት ቢተኛ፣ የወጋ መች እንቅልፍ አለው የጅምሩን ካልጨረሰው…” እንዳለውም ነው ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን፡፡

የአፍሪካ ህብረት የተመሠረበትን 50ኛ አመት ምክንያት በማድረግ በቻቺ ኢንተርናሽል አርቲስት ማናጅመንት የተሰናዳ የአፍሪካ ሙዚቃ ፌስቲቫል ግንቦት 3 እና 4 በሚሊኒየም አዳራሽ ይቀርባል፡፡ በአርቲስት ቻቺ ታደሠ በሚመራው ዝግጅት ላይ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከሰባት የአፍሪካ ሃገራት የተውጣጡ ሙዚቀኞች ተሳታፊ እንደሚሆኑ አዘጋጆቹ በጋዜጣዊ መግለጫቸው አስታውቀዋል፡፡ አርቲስት ቻቺ ታደሰ፤ ዝግጅቱን እንዲያደምቁ የ40 አገራት አርቲስቶችን ለመጋበዝ ብትሞክርም በኤምባሲዎች ትብብር የተሳካው የስድስት ሀገራት መሆኑንና ሂደቱ አድካሚ እንደነበር አመልክታለች፡፡

በዝግጅቱ ላይ ከኢትዮጵያ ሃይሌ ሩትስ እና ቺጌ ባንድ እንዲሁም ቻቺ ራሷ “I am an African” የሚለውን ዘፈኗን በመዝፈን ተሣታፊ እንደሚሆኑ ይጠበቃል፡፡ ለሁለት ተከታታይ ቀናት የሚካሄደውን የሙዚቃ ዝግጅት ፌስቲቫል ለመታደም ከጠዋቱ 3-12 ሰዓት ለሚቀርበው ለአዋቂዎች 50 ብር፣ ለህፃናት በነፃ ሲሆን ለምሽት የሙዚቃ ዝግጅቶች ለአንድ ሰው መግቢያ የ200 ብር ቲኬት መዘጋጀቱን አስተባባሪዎቹ አስታውቀዋል፡፡

የበይነ መረብ (internet) አጠቃቀምን አስመልክቶ የተዘጋጀው መጽሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ በዓለም ደገፋ እና ወንድወሰን አሰፋ የተዘጋጀው “በይነመረብ” የተሰኘ መጽሐፍ በዘርፉ ያሉትን የእንግሊዝኛ ቃላትና ሐረጐች በአማርኛ ቃላት ለመተካት የተሞከረበት ነው፡፡ አስራሰባት ምእራፎች ያሉት መጽሐፍ በበይነመረባዊ የቃላት መፍቻ የታገዘ ነው፡፡ ከ185 ገፆች በላይ ያሉት መጽሐፍ በ50 ብር እየተሸጠ ነው፡፡