Administrator

Administrator

“... እንግዲህ የእናቶች ጤና ሲባል በቅድሚያ እናቶችን ለጉዳት የሚዳርጋቸው የእናቶቹ ወደ ሆስፒታል ያለመምጣት ችግር ነው፡፡ ይህ ምክንያቱ የተለያየ ሲሆን አሁን አሁን ግን መንግስት የጤና ኤክስንሽን ሰራተኞችን ለህብረተሰቡ ቅርብ በሆነ ሁኔታ እያሰማራ እና እናቶቹም ስለጤናቸው እንዲማሩ እየተደረገ ስለሆነ የተሻለ ነገር አለ ማለት ይቻላል፡፡ ነገር ግን አሁንም ብዙ መስተካከል የሚገባቸው ነገሮች እንዳሉ አይካድም፡፡ እናቶች ለህክምና ወደሆስፒታል ሲመጡም አገልግሎት የሚሰጥባቸው መሳሪያዎች በበቂ ሁኔታ መገኘት ይገባቸዋል፡፡ የህክምናው ባለሙያ ክህሎትና የመሳሰሉት ሁሉ የእናቶችን ጤንነት ለመጠበቅ አንዱም ሳይዛባ በተሟላ መንገድ መገኘት ይገባቸዋል፡፡ ... የጤና ባለሙያው በቂ የሆነ ችሎታ ኖሮት በበቂ መሳሪያ እየታገዘ ህክምናውን እንዲሰጥ ሁኔታዎች መሟላት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህ ካልሆነ የእናቶች ወደሆስፒታል መምጣት አለመምጣት ምንም ልዩነት የለውም፡፡ ምናልባት ልዩነት ሊባል የሚችለው ወደሐኪም ሳይሄዱ ከእቤት መሞት ወይንም ሐኪም ቤት ሄዶ መሞት በሚል ሊገለጽ የሚችል ብቻ ነው...” ዶ/ር ታደሰ ኡርጌ /የጽንስና ማህጸን ሕምና እስፔሻሊስት የእናቶችና ሕጻናትን ሞት በመቀነስ ረገድ የደብረማርቆስ ሆስፒታል ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር እየሰራ መሆኑን ዶ/ር አብነት ሲሳይ በደብረማርቆስ ሆስፒታል የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት ገለጹ፡፡

እንደ ዶ/ር አብነት ገለጻ የደብረማርቆስ ሆስፒታል ከኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ጋር ከሚሰራው ስራ በተጨማሪ አይክ ኢትዮጵያ ከሚባል ግብረሰናይ ድርጅት ጋር በመተባበር የእናቶችን እና ሕጻናትን ጤንነት በሚመለከት ለሚሰራው ስራ ከተመረጡ ሁለት ሆስፒታሎች አንዱ ሆኖአል፡፡ ደብረማርቆስ ከአማራ ክልል ከትግራይ ደግሞ አድዋ ሆስፒታል ተመርጠው ከተወሰኑ ወራት ወዲህ ስራ የጀመሩ ሲሆን ከሕብረተሰቡ ጋር በተቀናጀ ሁኔታ መስራት አስፈላጊ በመሆኑ ንቃተ ህሊናን የማዳበር ስራ ተሰርቶአል፡፡ በጤና ተቋም ወይንም ወደ ሆስፒታል በመቅረብ የሚወልዱ እናቶች ቁጥር 20ኀ የማይሞላ በመሆኑ ይበልጡኑ እናቶችን ለማዳን ወደ ህብረተሰቡ መውረድ አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቶአል፡፡ ወደህብረተሰቡ ለመድረስ ደግሞ የጤና ኤክስንሽን ሰራተኞች ዋናዎቹ ድልድዮች በመሆናቸው በደብረማርቆስ ዙሪያ ያሉትን ሙያተኞች ጠርተን የፕሮግራሙን አላማ ከማስረዳት ጀምሮ የጤና ኤክስንሽን ሰራተኞቹ እናቶችን ከጤና ኬላ ወደ ጤና ጣብያ እንዲያስተላልፉ ከዚያም ከፍ ወዳለ ሆስፒታል የመቀባበልን ሁኔታ በተቀናጀና ስርአት ባለው መንገድ እንዲሰራ አስፈላጊ መሆኑን እንዲገነዘቡ በማድረግ ስራው ተጀምሮአል፡፡

እናቶች ብዙውን ጊዜ በእርግዝና ጊዜ ክትትል ሲያደርጉ ቢቆዩም ለመውለድ ወደሆስፒታል ወይንም ክትትል ሲያደርጉ ወደቆዩበት ጤና ተቋም የሚሄዱት በጣም ጥቂቶች የመሆናቸው ጉዳይ አሳሳቢ በመሆኑ ይህንን ሁኔታ መልኩን በመቀየር እናቶች በወሊድ ጊዜ ወደሆስፒታል ለመሄድ የሚያስችላቸውን ቅድመ ዝግጅት እንዲያደርጉ የሚያስችላቸውን ዘዴ መምከር ተገቢ ይሆናል፡፡ ይህንንም በተገቢው ለማስፈጸም እንዲያስችል ከኢሶግ እንዲሁም ከአይክ ጋር የሚሰራው ስራ የእርግዝና ክትትል ስታደርግ የቆየች እናት በመሀከል ብትሰወር ወደየት እንደደረሰች ፣ወልዳ ይሁን ወይንስ? በምን ምክንያት ? የሚለውን ለይቶ ማወቅና እናቶች ያሉበትን ሁኔታ በሚገባ ተረድተው ቅድመ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ለማስቻል የሚደረግ ክትትልን ይጨምራል፡፡ የደብረማርቆስ ሆስፒታል ከኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ጋር በመተባበር 5/ጤናጣቢያዎችን ባካተተ መልኩ የእናቶችንና የጨቅላዎችን ሞትና ደህንነት ሁኔታ በክትትል ይመዘግባል ፡፡ በዚህም መሰረት ከአንድ ወር በፊት ስለነበረው አሰራር በዶ/ር... ያለምወርቅ እንደቀረበው ሪፖርት ከሆነ በጤናጣቢያዎቹ ለሚኖረው አገልግሎት አንድ አምቡላንስ ተመድቦ አስፈላጊ በሆነበት ቦታና ሰአት እናቶችን ወደሆስፒታል ማመላለስ ተጀምሮአል፡፡ ሆስፒታሉ በየወሩ ከየጤናጣብያዎቹ ጋር በየወሩ በስብሰባ የሚገናኝ ሲሆን ችግሮችንም ከስር ከስሩ እየተከታተሉ መፍታት የሚያስችል አሰራር ተዘርግቶአል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ጤናጣብያዎቹ ለእናቶች ማበርከት ያለባቸውን አገልግሎት ጠንቅቀው እንዲያውቁና እንዲተገብሩ ለማስቻል ድጋፍ ይደረግላቸዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በየወሩ በሚኖረው ዳሰሳ የእናቶችን እና ጨቅላዎችን ሞት በተመለከተ በማዋለጃ አካባቢ ብቻ ሳይሆን በሆስፒታሉ በተለያዩ ክፍሎችም ያለው ሁኔታ በሪፖርት እንዲካተት ይደረጋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የእናቶችንና ጨቅላዎችን ሞት በመመዝገቡ ረገድ በሆስፒታሎችና በጤና ጣቢያዎች ያለውን ብቻም ሳይሆን እናቶች በቤታቸው እንዳሉ የተከሰተ ነገርም ካለ በቀበሌና በኤክስንሽን ሰራተኞች አማካኝነት እንዲመዘገብ የሚያስችል አሰራር ተዘርግቶአል፡፡ በደብረማርቆስ ሆስፒታል እንደውጭው አቆጣጠር በኦክቶበር ወር 150/አንድ መቶ ሀምሳ እናቶች የወለዱ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ ከጤና ጣብያዎች እስከ ሰማንያ ኪሎ ሜትር ከሚደርስ እርቀት በቅብብል የመጡና እራሳቸውም ወደ ሆስፒታሉ የመጡ ይገኙበታል፡፡ በአጠቃላይ ወደ 27 የሚሆኑ እናቶች ወደሞት አፋፍ ደርሰው የነበሩ ሲሆን ነገር ግን በሆስፒታሉ የተመዘገበ የእናቶች ሞት የለም፡፡ ለሞት አፋፍ እንዲደርሱ ከሚዳርጉዋቸው ምክንያቶችም አንዱ ደም መፍሰስ ሲሆን ሁለት እናቶች የማህጸን መተርተር የደረሰባቸው ናቸው፡፡ ሁለት እናቶች ደግሞ ከማህጸን ውጭ ያረገዙ ሲሆን ውርጃም የሚጠቀስ ነው፡፡ ከዚህ ውጭ እናቶች ከወለዱ በሁዋላ የሚከሰት የደም መፍሰስ አብዛኛውን ለሞት አፋፍ የመድረስ ሁኔታ ማለትም 25 በመቶ የሚሆነውን ድርሻ ይይዛል፡፡ ከእርግዝና ጋር ተያይዞ የሚከሰት የደም ግፊትም ያጋጠመ ሲሆን አስፈላጊውን ሕክምና በማግኘታቸው ከሞት ተርፈዋል፡፡ ከዚህ ውጭ የትራንስፖርት፣ የምግብ እጥረት እና የቤተሰብ እቅድ ዘዴን ባለመጠቀም ምክንያት እና ብዙ የወለዱ እናቶችም ለከፋ አደጋ ተጋልጠው ተገኝተዋል፡፡ ወደ ሀያ የሚሆኑ እናቶች በልጅነታቸው ግርዘት የተፈጸመባቸው ሲሆን በጎጂ ልማዳዊ ድርጊት ምክንያት በምጥ ጊዜ ለሚከሰቱ ሕመሞች የተጋለጡም አሉ ፡፡

ለሞት አፋፍ የደረሱ እናቶች እድሜ ከ20-40 የሚደርሱ ሲሆኑ የልጅነት ጋብቻም ለችግር ከሚያጋልጡ መካከል ናቸው፡፡ ከላይ የተጠቀሱትን ችግሮች ለመቅረፍም ህብረተሰቡን በማስተማሩ ረገድ በአቅራቢያው ያሉት የጤና ባለሙያዎች የበኩላቸውን ድርሻ ተወጥተዋል፡፡ በደብረማርቆስ ሆስፒታል የእናቶችን እና የጨቅላ ሕጻናትን ሞት ምክንያት ለማወቅ በሚደረገው አሰራር ያጋጠሙ ችግሮችን በሚመለከት የሕመምተኞች የቅብብል ሁኔታ አንዱ ሲሆን ሌላው የኤሌክትሪክ መስመር አለመኖር ነው፡፡ በማዋለድ ረገድ አንዳንድ ተጨማሪ መሳሪያዎች እንደቫኪዩም የመሳሰሉ ማለት ነው እጥረቱ እንዳለ ተገንዝበናል፡፡ ነገር ግን መፍትሔውን በሚመለከት አንዳንድ ጤና ጣቢያዎች ያለባቸውን የቅጽ እጥረት እራሳቸው በመፍጠር ተገቢውን መረጃ አያይዞ ወደሆስፒታል የመላክ አሰራር ተጀምሮአል፡፡ የኤሌትሪክ አገልግሎትንም በሚመለከት ለአንዳንድ ጤና ጣቢያዎች በቻርጀር የሚሰራ መብራት ለመስጠት ሁኔታዎች ተመቻችተዋል፡፡ የህክምና መርጃ መሳሪያዎችም በተቻለ መጠን በጎደለበት ቦታ እንዲሰጥ ሆስፒታሉ የራሱን መፍትሔ ዘርግቶአል፡፡ በአጠቃላይም ከጤናጣቢያዎቹ ጋር በወር አንድ ጊዜ አጠቃላይ ስብሰባ የሚደረግ ሲሆን በሆስፒታሉ ከሰራው ጋር የሚገኛኙት የሚመለከታቸው ባለሙያዎች በሙሉ ወደጤናጣቢያዎች እየወረዱ የጎደለውን ነገር የማየት ስራ እንዲሰራ ከስምምነት ተደርሶአል፡፡ ከሆስፒታሉ ጋር በትብብር የሚሰሩ ሳላይት ጤና ጣቢያዎችን በምን መንገድ ማጠናከር እንደሚገባ እና ያለውን ክፍተት ማሟላት እንዲሁም ምላሾችን በተገቢው በመመርመር አስፈላጊውን ማድረግ በሆስፒታሉ የተዋቀረው ቡድን ስራ መሆኑ የታመነበት ስለሆነ የእናቶችንና ጨቅላዎችን ሞት ምክንያት ከማወቅ አንጻር የበኩሉን አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ እሙን ነው እንደ ዶ/ር ያለምወርቅ፡፡

የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ከአለምአቀፉ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ጋር በመተባበር በሚያደርገው እገዛ በኢትዮጵያ ከ9/መንግስታዊ ሆስፒታሎችና 45/ ጤና ጣብያዎች ጋር በመተባበር የእናቶችን ሞት ሁኔታ ለማወቅ ለሚሰራው ስራ እንዲረዳ በየሆስፒታሎች መረጃ ለመሰብሰብ እንዲያስችል አንዳንድ ኮምፒዩተር ገዝቶ አከፋፍሎአል፡፡ ዶ/ር አብነት ሲሳይ ከደብረማርቆስ ሆስፒታል የኮምፒዩተሩን አገልግሎት ሲገልጹ ከአሁን ቀደም ባለው አሰራር የህመምተኞች ካርድ በአካል የሚቀመጥ ሲሆን ከቦታ ጥበት የተነሳ ከተወሰነ ጊዜ በሁዋላ እንዲቃጠል ይደረጋል፡፡ አሁን ግን ኮምፒዩተሩን በማግኘታችን ...ለምሳሌ የዛሬ ሶስት አመት አንዲት እናት ታክማ የነበረ እና ሐኪሙዋ በሌለበት እንደገና ለሕክምና ብትመለስ በኮምፒዩተር የተያዘ መረጃ ካለ በቀላሉ ችግርዋን ለመረዳት እና በወቅቱ ባለው ሐኪም ለመረዳት ትችላለች፡፡ ስለዚህ የህሙማኑን መረጃ በተሙዋላ መንገድ ለረጅም ጊዜ ለማስቀመጥ የሚረዳ በመሆኑ ጠቀሜታው የጎላ ነው ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያውያን ስደተኞችና እግር ኳስ በደቡብ አፍሪካ
በደቡብ አፍሪካ በስደት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በርካታ ናቸው። የ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ድል እንዲቀናው ስታዲየም ገብተው ድጋፋቸውን በመስጠት ከፍተኛ እንቅስቃሴ አድርገዋል፡፡ ድጋፍ አሰጣጣቸውም ከጨዋታው ቀጥሎ የዓለም አቀፍ ብዙሃን መገናኛውን ቀልብ ከሳበ ጉዳይ አንዱ ሆኖ አልፏል፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጣ የስፖርት አምድ አዘጋጅ ግሩም ሰይፉ በደቡብ አፍሪካ ጨዋታዎቹ በተካሄዱበት ስታዲየም ተገኝቶ ከጥቂቶቹ ኢትዮጵያውያን ጋር እንዴት ደቡብ አፍሪካ እንደገቡ፣ ስለሚገኙበት ሁኔታ እና ስለሰጡት ድጋፍ ጠይቋቸው እንደሚከተለው መልሰዋል፡፡
“ኤርትራዊ ብሆንም ዋልያዎቹን ደግፌአለሁ”
ሰናይ ነጋ

የተወለድኩት በደሌ የሚባል ስፍራ ኢሊባቡር ውስጥ ነው፡፡ከልጅነቴ ጀምሮ ኳስ ስለምወድ እጫወትም ነበር፡፡የአንደኛ ደረጃ ትምህርቴን እዚያው ኢሊባቡር ውስጥ ተማርኩ፡፡ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን ደግሞ በአየር ጤና እና በቦሌ ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተከታትያለሁ፡፡በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል በተነሳው ግጭት ኤርትራዊ በመሆኔ ከቤተሰብ ጋር ወደ ኤርትራ ሄድኩ፡፡ኤርትራ የገባሁት የ23 ዓመት ወጣት ሆኜ ነበር፡፡ በኤርትራ ለ11 ዓመታት በውትድርና ቆየሁ፡፡
የውትድርና ህይወት ሲያማርረኝ በሽሬ በኩል አቋርጬ ወደ ኢትዮጵያ ተመለስኩ፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ እህቴ ስለነበረች እርሷ ጋር ለ15 ቀናት ቆየሁ፡፡
ከዚያ በኋላ በሞያሌ አድርጌ ናይሮቢ ገባሁ፡፡ከሁለት ዓመት የናይሮቢ ቆይታ በኋላ በአውሮፕላን ደቡብ አፍሪካ ገብቼ እዚህ ከነበሩ ቤተሰቦቼ እና ጓደኞቼ ጋር ተቀላቀልኩ፡፡ ከዚያን ጊዜ ወዲህ በንግድ ሥራ ተሰማርቼ እየሠራሁ ነው፡፡ኳስ ጨዋታ ብዙም አልከታተልም ነበር፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ወደ ደቡብ አፍሪካ ሲመጣ ግን እዚህ ካሉ ኢትዮጵያውያን ጋር ስለምሠራ፣ የነበረው መንፈስ ግጥሚያቸውን እንዳይና ቡድኑን ለመደገፍ አነሳሳኝ፡፡ዜግነቴ ኤርትራዊ ቢሆንም የተወለድኩበት ያደግኩበት እና የተማርኩበት አገር ኢትዮጵያ ስለሆነች “ዋልያዎቹን” ደስ ብሎኝ ደግፌአለሁ፡፡

* “Conversation with God” የሚለው መፅሃፍ “እግዚአብሄር ፖለቲከኛ ነው” ይላል * ምርጫ ቦርድ “ሆደሰፊ” እየሆንኩ ነው ብሏል (እንመነው እንዴ?) ዛሬ ከናንተ ምን እንደምፈልግ ታውቃላችሁ? የኢህአዴግን “ትዕግስት” እና የምርጫ ቦርድን “ሆደሰፊነት” ብቻ! (ራሳቸው ሲናገሩ ሰምቼ እኮ ነው!) ሁለቱ አለን የምትሉ ከሆነ ግን በነፃነት ማውጋት፤ አዳዲስ ምስጢሮችን መለዋወጥ፤ ፖለቲከኞችን ማማት፤ ባለሥልጣናትን “መቦጨቅ” (ማስረጃ ባይኖረንም በመረጃ) እንችላለን፡፡ እንዳልኳችሁ እናንተ ብቻ ትዕግስቱና ሆደ ሰፊነቱ ይኑራችሁ፡፡ እኔ የምለው ግን--- ሰሞኑን ምርጫ ቦርድ “ሆደሰፊነቱን” በኢቴቪ ሲናገር ሰምታችኋል? (የአበሻ ይሉኝታ አያውቅም ልበል?) ከኢህአዴግ ጋር የፓርቲዎች ምክር ቤት አባል የሆኑ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የእጩዎች ማስመዝገቢያ ጊዜ እንዲራዘምላቸው ጠይቀው፤ በአስር ቀን አራዘምኩ ብሎ እኮ ነው “ሆደ ሰፊ ነኝ” ያለው (ሆደ ሰፊ አያውቅም ማለት ነው!) ባለፈው ሳምንት የኢህአዴግ ፅ/ቤት ሃላፊ የሆኑት አቶ ሬድዋን ሁሴን ከምርጫው ጋር በተገናኘ ስለተቃዋሚዎች ያሉትን ሰምታችኋል አይደል? (ኢህአዴግ ግን አሳዘነኝ!) በምርጫው ይሸነፋል ብዬ እንዳይመስላችሁ! (መታሰቡስ!) በነገራችሁ ላይ አንድ ፖለቲከኛ ወዳጅ አለኝ --- ሁሌ ምርጫ ሲቃረብ “አስማተኛ ፓርቲዎች ካልተፈጠሩ በስተቀር ኢህአዴግ በምርጫ አይሸነፍም!” ይለኛል (የሚያውቀው ነገር ቢኖር ነው) አስማቱን ትተን ወደ ነባራዊው እውነታ ስንመጣ --- አቶ ሬድዋን ምን ነበር ያሉት? “የተቃዋሚዎች በምርጫው መሳተፍና አለመሳተፍ ትርፍም ኪሳራም የለውም” በዚህ አነጋገራቸው የበሸቀ ሌላ ወዳጄ “የሳቸውም ንግግር ያው ነው!” አለኝ - በንዴት ጨሶ (ትርፍም ኪሳራም የለውም ማለቱ እኮ ነው!) አንድ ታዋቂ የአገር ውስጥ የፖለቲካ ተንታኝ በሰጡት አስተያየት ደግሞ “ንግግሩ ለሃያ አንድ ዓመት በሥልጣን ላይ ለቆየ ፓርቲ አይመጥንም” ብለዋል፡፡

ደግነቱ ይሄን አስተያየት በሰጡ ማግስት ነፃ የትምህርት እድል አግኝተው ወደ አሜሪካ መብረራቸውን ሰምቻለሁ (አሜሪካ የመሸጉ ፖለቲከኞቻችን ስንት ደረሱ ይሆን?) እኔ የምለው ግን--- ኢህአዴግ መቼ ይሆን ዲፕሎማት የሚዋጣለት? (ከዚህ በኋላማ ተስፋ የለውም-- አረጀ እኮ!) አሁን እንግዲህ ለየት ወዳለው የዛሬ አጀንዳችን ብወስዳችሁ ሳይሻል አይቀርም፡፡ ሰሞኑን እጄ ገብቶ ያነበብኩት መፅሃፍ በአንድ አሜሪካዊ ደራሲ የተፃፈ ነው፡፡ እሱ ግን እኔ አልፃፍኩትም ባይ ነው፡፡ (ከደሙ ንፁህ ነኝ ለማለት ይመስላል) እንዴት ሲባል----እግዚአብሄር የነገረኝን በወረቀት ላይ ከማስፈር ውጭ ሌላ ሚና የለኝም ይላል፡፡ ኒል ዶናልድ ዋልሽ የተባለው አሜሪካዊ ደራሲ ከእግዚአብሔር ጋር ያደረግሁት ንግግር ነው ያለው መፅሃፍ ባለ ሦስት ጥራዞች ሲሆን ርዕሱም Conversation with God ይላል፡፡ (ከእግዚአብሔር ጋር የተደረገ ወግ ወይም ጨዋታ ልትሉት ትችላላችሁ) ምልልሳቸውን ስታነቡት ግን ምኑም ጨዋታ አይመስልም፡፡ የጦፈ Hard talk ነው፡፡ በነገራችሁ ላይ ደራሲው ከእግዚአብሄር ጋር ንግግር የጀመረው ድንገት ነው - ሳያውቀው፡፡ በፈረንጆቹ 1993 የፋሲካ በዓል አካባቢ በህይወቴ አስደናቂ ክስተት ተከሰተ ይላል - ደራሲው፡፡ በወቅቱ በግል ህይወቱ፣ በሙያውና በሥነልቦናው ደስተኛ አልነበረም፡፡ ህይወቴ ሁሉ የከሸፈ ይመስለኝ ነበር (እንደኢትዮጵያ ታሪክ ይሆን?) የሚለው ደራሲው፣ የተሰማውን ስሜት በደብዳቤ ላይ እያሰፈረ የማስቀመጥ የዓመታት ልማድ እንደነበረው ገልጿል አንድ ቀን ግን (ሳይመረው አልቀረም ) የተለየ ደብዳቤ መፃፍ ጀመረ - በቀጥታ ለእግዚአብሄር፡፡ ደብዳቤው የቁጣ፣ የምሬት፣ የንዴት፣ የመወነባበድና የወቀሳ ነበር፡፡ ልክ የሚፅፈውን ሁሉ ፅፎ ሲጨርስ ነው ከእግዚአብሄር ጋር ግንኙነት የጀመረው - በመፅሃፉ መግቢያ ላይ እንደገለፀው፡፡ መጀመርያ ላይ መደነጋገጥና መደነጋገር እንደተፈጠረበት ደራሲው ባይካድም፣ በኋላ ግን እንደጓደኞች ያወሩ እንደነበር ይናገራል - ለአንድ ቀን ሳይሆን ለሶስት ዓመት፡፡ እውነት ለመናገር ወጋቸው ፈፅሞ እኮ የፈጣሪና የሰው አይመስልም፡፡

ሰውና ሰው የሚተጋተግ እንጂ ፡፡ የእግዚአብሔርም ምላሽ የማይታመን ነው፡፡ ተጠራጥሬው ነበር ይለናል - ደራሲው፡፡ ወዲያው ግን ራሱ እግዚአብሄር መሆኑን ተረድቼ ሶስት ዓመት አብረን ዘለቅን፡፡ እኔ እጠይቃለሁ፣ እሱ ይመልስልኛል፡፡ የውይይታቸውም ውጤት Conversation with God የሚለውን መፅሃፍ ወለደ፡፡ መፅሃፉ ታትሞ ለገበያ ሲቀርብም ተወዳጅ በመሆን እንደተቸበቸበ ይናገራል - ኒል ዶናልድ ዋልሽ፡፡ የኒውዮርክ ታይምስ Bestseller ነበር፡፡ በነገራችሁ ላይ እግዚአብሔር ከአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች ጆርጅ ቡሽን፣ ቢል ክሊንተንና ጂሚ ካርተንን እንደሚያደንቃቸው ለደራሲው ነግሮታል - Conversation with God በተሰኘው መፅሃፍ፡፡ ያለምክንያት ግን አይደለም፡፡ ለአገራቸውና ለዓለም ባከናወኑት ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ሥራዎቻቸው እንደሆነ አስረድቶታል፡፡ እግዚአብሔር ሌላው የሚያደንቀው መሪ ማን መሰላችሁ? የሶቭየቱ ሚኻኤል ጐርባቾቭ! ለምን? ቀዝቃዛውን ጦርነት ማስቆም የቻሉና ብቸኛው ኮሙኒስት የሰላም የኖቤል ተሸላሚ ሲል አድንቋቸዋል - እግዚአብሔር በመፅሃፉ ላይ፡፡ ለነገሩ ትክክለኛው የዓለም ስርዓት ኮሙኒዝም ነው ብሏል ለደራሲው ሲያወጋው - ነገር ግን አተገባበር ላይ ችግር አለ ባይ ነው (የሰው ልጅና ኮሙኒዝም አልተግባቡም እንደማለት) የእግዚአብሄርን ኮሙኒስትነት አስረግጦ መናገር ባይቻል እንኳን ካፒታሊስት እንዳልሆነ በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል፡፡ እንዴት ቢሉ---- በውይይታቸው ላይ የዓለም ሃብት እኩል መከፋፈል አለበት የሚል ሃሳብ ይሰነዝራል - እግዚአብሄር፡፡ እንዳልኳችሁ በመፅሃፉ ውስጥ ደራሲውና እግዚአብሔር ያላነሱትና ያልተከራከሩበት ጉዳይ የለም፡፡ ስለ ትዳር፣ ፍቅር፣ ወላጅነት፣ ታክስ፣ ስለሰይጣንና ሲኦል (ሰይጣንና ሲኦል የሰው ልጅ ፈጠራዎች ናቸው ብሏል) ከሞት በኋላ ስላለው ህይወት፣ ወዘተ በዝርዝር ተወያይተዋል፡፡

የአሁኑ ዘመን ትውልድ ራሱ ከልጅነት ሳይወጣ ልጅ አሳዳጊ መሆኑን ይወቅስና፣ የሰው ልጅ 40 ዓመት ሳይሞላው በፊት ወላጅ መሆን አይገባውም በማለት ልጆችን ማሳደግ የሚገባቸው አያቶች እንደሆኑ ይጠቁማል፡፡ ዓለም ጦርነት የሌለባት ሰላማዊ ፕላኔት ትሆን ዘንድ ምን ይደረግ ለሚለውም ሰፊ መልስ ይሰጣል - እግዚአብሄር፡፡ እስቲ የደራሲውና የእግዚአብሄር ውይይት ምን እንደሚመስል ለማየት ትችሉ ዘንድ አለፍ አለፍ እያልኩ ላስነብባችሁ፡፡ ደራሲ -እባክህ --- አገራት ከአገራት ጋር ሰላም የሚያወርዱበትንና ጦርነት ከነአካቴው የሚገታበትን መንገድ ንገረኝ --- እግዚአብሔር - በአገራት መካከል ሁልጊዜም አለመስማማት መኖሩ አይቀርም፡፡ አለመስማማት ችግር የለውም፡፡ እያንዳንዱ አገር ልዩ መሆኑን የሚያሳይ ጤናማ ምልክት ነው፡፡ አለመስማማትን በኃይል መፍታት ግን ከፍተኛ ያለመብሰል ምልክት ነው፡፡ በዓለም ላይ የሃይል መፍትሄ የማይወገድበት ምክንያት የለም፣ አገራቱ ለማስወገድ ፈቃደኛ እስከሆኑ ድረስ ነው ታዲያ፡፡ አንዳንዶች በገፍ የሚሞቱት ሰዎችና የሚጠፋው ህይወት ይሄንን ፈቃደኝነት ለማምጣት በቂ ነው ብለው ሊያስቡ ይችላሉ፡፡ ኋላ ቀር ባህል ለሰፈነበት እንዳንተ ያለው አገር ግን ነገሩ እነሱ እንደሚያስቡት አይደለም፡፡ ሙግት ማሸነፍ እችላለሁ ብለህ እስካሰብክ ድረስ መሟገትህ አይቀርም፡፡ በጦርነት ማሸነፍ እችላለሁ ብለህ እስካሰብክ ድረስም ትዋጋለህ፡፡ ደራሲ - ለዚህ ታዲያ መፍትሄው ምንድነው? እግዚአብሔር - መፍትሄ የለኝም፡፡ ምልከታ እንጂ! --- የአጭር ጊዜ መፍትሄ የሚሆነው አንድ የዓለም መንግስት መመስረት ነው - አለመግባባቶችን የሚፈታ የዓለም ፍርድ ቤት ያለው! (አሁን እንዳለው ዓለማቀፍ ፍ/ቤት ውሳኔው ችላ የማይባል መሆን ግን አለበት) የትኛውም አገር የቱንም ያህል ጉልበት ቢኖረውና ተፅዕኖ ማሳረፍ ቢችልም ሌላው አገር ላይ ጥቃት እንዳይሰነዝር ዋስትና የሚሆን አንድ የዓለም ሰላም አስከባሪ ኃይል ሊመሰረት ይችላል፡፡

… በዚህ መንገድ ብቻ ነው በዓለም ላይ ሰላም ሊሰፍን የሚችለው፡፡ ያኔ --- የትናንሽ አገራት ዕጣ ፈንታ በትላልቅ አገራት መልካም ፈቃድ ላይ የተመረኮዘ መሆኑ ይቀራል፡፡ በራሳቸው ሃብት ላይ መደራደራቸው ያቆማል፡፡ ቁልፍ መሬታቸውን ለውጭ ወታደራዊ ሃይል (ቤዝ) አሳልፈው አይሰጡም፡፡ … አንድ አገር ብትወረር 160ዎቹም የዓለም አገራት በተቃውሞ ይነሳሉ፡፡ --- ትላልቅ አገራት የዓለምን የሃብት ክምችት ለብቻቸው መቆጣጠርና ማከማቸታቸውም ይቀራል፡፡ ይልቁንም ሃብቱን ለሌሎች አገራት እኩል እንዲያካፍሉ---ይገደዳሉ፡፡ የመላው ዓለም መንግስትም የጨዋታውን ሜዳ ለሁሉም እኩል ያደላድላል፡፡ (ደራሲውና እግዚአብሄር ስለዘመኑ የትምህርት ሥርዓትም የጦፈ ክርክር አድርገዋል፡፡ ቀንጨብ አድርጌ ላስነብባችሁ! ) ደራሲ - ስለትምህርት ልትነግርኝ ትፈቅዳለህ? እግዚአብሔር -- እንዴታ! አብዛኞቻችሁ የትምህርትን ትርጉም፣ ዓላማና ጥቅም በትክክል አልተረዳችሁትም፡፡ የትምህርት አሰጣጥ ሂደትንማ ባናነሳው ይሻላል፡፡ ---- አብዛኛው የሰው ዘር የትምህርት ትርጉምና ዓላማ እንዲሁም ጥቅም ዕውቀት ማስተላለፍ ነው ብሎ ደምድሟል፡፡ አንድን ሰው ማስተማር ማለት - የአንድን ቤተሰብ፣ ጐሳ፣ ህብረተሰብ፣ አገር፣ ዓለም የተከማቸ ዕውቀት መስጠት ሆኗል! ሆኖም ትምህርት ከዕውቀት ጋር እምብዛም የሚያገናኘው ነገር የለም፡፡ ደራሲ -ትምህርት ከዕውቀት ጋር ካልተገናኘ ከምን ጋር ነው የሚገናኘው ታዲያ? እግዚአብሔር - ከጥበብ፣ ከብልሃት ደራሲ-ልዩነታቸው ምንድነው? እግዚአብሔር- ጥበብ ወደ ኑሮ የተቀየረ እለት በእለት የተቀየረ ዕውቀት ነው፡፡ -- ለልጆቻችሁ ዕውቀት ስትሰጧቸው ምን ማሰብ እንዳለባቸው እየነገራችኋቸው ነው፡፡ ማወቅ ያለባቸውን ነው የምትነግሯቸው፤ እውነትን ነው እንዲረዱ የምትፈልጉት፡፡ ጥበብ ስትሰጧቸው ግን ማወቅ ያለባቸውን ወይም እውነቱን አይደለም የምትነግሯቸው፡፡ ይልቁንም የራሳቸውን እውነት እንዴት እንደሚያገኙ ታስተምሯቸዋላችሁ፡፡ ደራሲ -ግን እኮ ያለ ዕውቀት ጥበብ ሊኖር አይችልም፡፡ እግዚአብሔር - እስማማለሁ፡፡

ለዚህ እኮ ነው ጥበብ ሰጥታችሁ ዕውቀትን መዘንጋት የለባችሁም ያልኩት፡፡ የተወሰነ መጠን ዕውቀት ከአንደኛው ትውልድ ወደ ቀጣዩ መተላለፍ አለበት፡፡ በተቻለ መጠን ግን ትንሽ ቢሆን ይመረጣል፡፡ የቀረውን ህፃኑ ፈልጐ ያግኘው፡፡ ዕውቀት ይረሳል፤ ጥበብ ግን ፈፅሞ የሚረሳ አይደለም፡፡ ደራሲ - ስለዚህ ት/ቤቶቻችን ትንሽ ትንሽ ማስተማር ነው ያለባቸው ማለት ነው? እግዚአብሔር - ት/ቤቶቻችሁ አትኩሮታቸውን መለወጥ አለባቸው፡፡ አሁን በእጅጉ ያተኮሩት ዕውቀት ላይ ነው፡፡ ለጥበብ ትንሽ የተቆጠበች ትኩረት በመስጠት፡፡ በትንታኔያዊ አስተሳሰብ፣ በችግር መፍታትና በሎጂክ ዙርያ የሚሰጡ ትምህርቶች ለብዙ ወላጆች አስፈሪ ናቸው፡፡ እንዲህ ዓይነቶቹ ትምህርቶች ከካሪኩለሙ እንዲወጡ ይሻሉ፡፡ እንዲህ የሚያደርጉት የራሳቸውን የአኗኗር ዘይቤ ጠብቀው ለማቆየት ነው፡፡ እንዴት ቢሉ … የራሳቸውን ሳይንሳዊ የአስተሳሰብ ስልት እንዲያዳብሩ የተፈቀደላቸው ህፃናት የወላጆቻቸውን ሥነ ምግባርና አጠቃላይ የኑሮ ዘይቤ መከተል አይፈልጉም፡፡ የአኗኗር ዘይቤያችሁን ጠብቃችሁ ለማቆየት ስትሉ የትምህርት ስርዓታችሁ የህፃናትን ችሎታ ሳይሆን ትውስታቸውን ብቻ እንዲያዳብር አድርጋችሁ ነው የቀረፃችሁት፡፡ እንግዲህ የቀረውን መፅሃፉን ፈልጋችሁ አንብቡት፡፡ እኔ ግን አንድ ነገር በጣም ተመኘሁ--- እንደዚህ አሜሪካዊ ደራሲ ከእግዚአብሄር ጋር የመወያየት እድል ባገኝ አልኩ ለራሴ፡፡ ስለአገሬ ፖለቲከኞች ብዙ ብዙ የምጠይቀው ነገር ስላለኝ እኮ ነው፡፡ የዘመናት የፖለቲካ እንቆቅልሻችን እንዴት እንደሚፈታ ብልሃቱን ይሰጠኝ ዘንድም መወትወቴ አይቀርም ነበር፡፡ የእኛ የፖለቲካ ችግር ሰው ሰራሽ ቢሆንም መፍትሄው በሰው አቅምና ችሎታ የማይገኝ መሆኑን አይተነዋላ!

ሺጉሜን የተባለው የጃፓን ንጉሥ ቻ-ኖ-ዩ የተባለው የሻይ ስነስርዓት በጣም ደስ ይለው ነበር፡፡ በችሎቱ ላይ ዳኛ ሆኖ ሲቀመጥ እንኳ ሻዩን እያደቀቀ ይፈጭ ነበር ይባላል፡፡ ምክንያቱ የሚከተለው ነው፡- 

ከዕለታት አንድ ቀን የሻይ ነጋዴ የነበረ ወዳጁን
“ህዝቡ ስለ እኔ ምን ያስባል?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ነጋዴውም፤
“ማስረጃቸውን በግልፅ የማያቀርቡ ሰዎችን ትቆጣለህ፡፡ ሙልጭ አድርገህም ትሳደባለህ የሚል አስተያየት ነው ያለው፡፡ በዚህ ምክንያትም ህዝቡ እውነተኛውን ህጋዊ ማንነቱንና ጉዳዩን ወደ አንተ ለማቅረብ ስለሚፈራ እውነቱ በግልፅ አይታወቅም” ሲል ይነግረዋል፡፡
ንጉሡም፤
“አመሰግናለሁ! እንኳን ነገርከኝ፡፡ እኔ እስከዛሬ፤ ለሰዎች እቅጩን የመናገር ልማድ ነበረኝ፡፡ ስለዚህም ትሁቶቹና በድፍረት በአደባባይ የመናገር ድፈረት የሌላቸው ጨዋ ሰዎች እውነቱን ፍርጥ አድርገው አይገልፁም፡፡ ወደፊት ጠባዬን ማረም ይኖርብኛል” ይላል፡፡
ከዚህ በኋላ ንጉሡ ዙፋን ችሎት በሚቀመጥበት ጊዜ ሁሉ፤ አንድ የሚያስገርም ነገር ማድረግ ጀመረ ይባላል፡፡ በጨርቅ ተሸፍኖ የሻይ መውቀጫው/መፍጫው ከስሩ እንዲቀመጥለት ያዛል፡፡ በሀር ጨርቅ ተሸፍኖ ጥዋ መስሎ ይቀመጥለታል፡፡ ከዚያም አቤቱታ አቅራቢው ህዝብ አቤቱታውን ሲያሰማ እሱ ሻዩን እየወቀጠ ትኩረቱን ወደ ሙቀጫው በማድረግ ቁጣውን ይቆጣጠራል፡፡
ቀጥሎም የፈጨውን ሻይ በትክክል መድቀቅ አለመድቀቁን በእጁ እየነካ ያየዋል፡፡ ያረጋግጣል፡፡ ሻዩ በትክክል ከተፈጨ መንፈሱ የረጋና ሚዛናዊ መሆኑን ያስባል፡፡ በትክክልም አቤቱታ ማዳመጡን ያምናል፡፡ ሻዩ ያላግባብ የተወቀጠ ከሆነ ግን የተረበሸና ቁጠኛ ስሜት እንደነበረው ያውቃል፡፡
በረጋ መንፈስ የተፈጨው ሻይ፤ ፍርድ በትክክል መስጠቱንና አቤት ባዮቹም ረክተው መሄዳቸውን ይነግረዋል፡፡ ይሄኔ፤
“ተመስገን! ህዝቤ ሳያዝንብኝ፤ ረክቶና ደስ ብሎት ሄዷል ማለት ነው” ብሎ ፈገግ ይላል፡፡
* * *
ለህዝብ የሚቆረቆር ዕውነተኛ መሪ የህዝብን ብሶት ማዳመጥ፤ አቤቱታውን መስማት ያረካዋል። ህዝብ የልቡን ዕውነት የሚደብቅ ከሆነ ትክክለኛ አስተዳደር አለ ለማለት ያዳግታል፡፡ ዐይና - ውጣው በአደባባይ እንደልቡ ሲናገር፤ ጭምቱና ፈሪው ሃሳቡን ሳይገልጽ ይቀራልና ሥርዓቱ ሁሉንም ያስተናግዳል ለማለት አያስደፍርም፡፡ ሃሳቡን የሚገልጽ ህዝብ የዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ምሰሶ ነው። በዚህ ረገድ በጥሞና የህዝብን የልብ ትርታ ለማዳመጥ የሚችል ጆሮ ያለው መሪ ያስፈልጋል፡፡ የመሥሪያ ቤት አለቃ፣ የማህበር መሪም ሆነ የፖለቲካ መሪ አስተዋይ አዕምሮ፣ ሆደ - ሰፊ አመራርና “ወደፊት ይህን ይህን ጠባዬን ማረም ይኖርብኛል” የማለት ድፍረት ሊኖረው ያሻል፡፡ ያን ካገኘን ታድለናል፡፡
የአንድ ሀገር ህዝብ እንደዜጋ የተፃፈን ጽሑፍ በነፃነት፣ በጥሞናና በጥንቃቄ አንብቦ የሚመረምር፤ ያሻውን ዓይነት የፖለቲካ ሥርዓት የሚከተል፣ በነፃነት አገዛዙን የሚቃወም፣ የሚተችና ሲያስፈልግ አይሻኝም የማለት መብቱን የሚያውቅ ሊሆን ይገባል፡፡ እንደአራሽ እንደላብ - አደርም የአቅሙን ያህል ማምረትና የኢኮኖሚ ህልውናውን ሊያጠናክር ይጠበቅበታል፡፡ እንደዜጋም ሆነ እንደሠራተኛ በአገሩ ይኖር ዘንድ የሚያሠራው፣ የሚያሳትፈው ሥርዓትና ህግ ሊያገኝም የግድ ነው፡፡
“ባገር እኖር ብዬ
ልጅ አሳድግ ብዬ
ከብት እነዳ ብዬ፤
ለባሻ ዳርኩለት ሚስቴን እቴ ብዬ”
እያለ የሚያለቅስ ባላገር በምንም ዓይነት ማየት የለብንም፡፡ ጊዜውም ቦታውም አይፈቅድምም። በፖለቲካ የተገፋ፣ በኢኮኖሚ የደቀቀ፣ ማህበራዊ ድርና ማጉ ውሉ የጠፋ ህብረተሰብ እንዳይኖር ነው የስትራቴጂያችን ዒላማ! ውሃ ጋ ከሆን አሣ፣ ግጦሽጋ ከሆን ሥጋ መብላትን ልናውቅበት ወቅቱ ያስገድደናል፡፡
አንድ የገዛ በሬው ሊወጋው የሚያሳድደው ባለበሬ ለአንድ የሰፈር አዛውንት፤ “እረ ይሄ በሬ እያሳደደ አስቸገረኝ“ ቢላቸው፤ “የት ነው የምትተኛው?” ብለው ጠየቁት አሉ፡፡ ባለበሬውም፤ “ቤቴ። ሣር ፍራሼ ላይ!” ይላቸዋል፡፡ ሽማግሌውም፤
“ታዲያ ቀለቡ ላይ እየተኛህ ዱሮስ ላያባርርህ ኖሯል እንዴ?” አሉት ይባላል፡፡ ሰውንም ቀለቡ ላይ ተኝተን ነፃነት አለህ ብንለው የለበጣ ነው የሚሆነው፡፡ ነፃነቱን ከኢኮኖሚ ጥቅሙ የሚያስተሳስር ሥርዓት መፍጠር ተገቢ ነው፡፡ ለተገቢ ሥርዓት ክሳቴ የሚታገሉ ሁሉ ጊዜን መሠረት ያደረገ ስትራቴጂ ይኖራቸው ዘንድ ወቅቱ ይጠይቃቸዋል፡፡
“ፊት የበቀለን ወፍ ይበላዋል” የሚለውን ተረት ሳንረሳ “የዘገየ ፍርድ ካልተፈረደ አንድ ነው”ን እያውጠነጠንን፤ ትክክለኛው ጊዜ ሲደርስ ግን “የሚሥማሩን አናት መምታት”ና አጋጣሚን በአግባቡ መጠቀም ወሳኝ መሆኑን ልናሰምርበት ይገባል፡፡ በወቅቱ ያልዘራም በወቅቱ ያልሰበሰበም ሁለቱም ከመራብና ከማስራብ አይድኑም - “ንገሥ ቢሉት ዛሬ ሰምበት ነው አለ” የሚለው የጉራጊኛ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው!!

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ በድጋሚ ተቀጠረ

በዓዲ ኀትመትና ማስታወቂያ ሓላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ስም እየታተመ የሚወጣው “አዲስ ታይምስ” መጽሔት፤ ከብሮድካስት ባለሥልጣን የሞያ ብቃት ማረጋገጫ ምስክር ወረቀት እድሳት በመከልከሉ ከኅትመት ውጪ ሆነ፡፡ አሳታሚው ለዝግጅት ክፍላችን እንደገለጸው፤ የአገሪቱ የፕሬስ ሕግ በሚያዘው መሠረት የመጽሔቱን ዓመታዊ ፈቃድ ለማሳደስ ከድርጅቱ የሚጠበቁትን መስፈርቶች ሙሉ በሙሉ ቢያሟላም የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን ጥር 2 ቀን 2005 በላከው ደብዳቤ ለመጽሔቱ የሞያ ብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት እድሳት እንደማያደርግ አስታውቋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን እድሳቱን እንደማያደርግ ለአሣታሚው በላከው ደብዳቤ ያመለከተው ሦስት ዋና ዋና ምክንያቶችን በመጥቀስ ነው። እነዚህም የአክስዮን ባለቤቶችና የአድራሻ ለውጥ ሲደረግ በ15 ቀን ውስጥ ለባለሥልጣኑ ማሳወቅ አለመቻል፣ ለኢትዮጵያ ቤተ መጻሕፍት መወዘክር የዐሥራ አምስት ቀን እትም አለማስገባት እንዲሁም መፅሔቱ “በሕጋዊ ባለቤቶቹ ሳይሆን ምንጩ በማይታወቅ ገንዘብ ነው የሚተዳደረው የሚሉት ናቸው፡፡ የ“አዲስ ታይምስ” መፅሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ተመስገን በበኩላቸው፤ የአክስዮን ባለቤትነት እና የአድራሻ ለውጥ ሲያደርጉ በጊዜው በደብዳቤ ማሳወቃቸውን፣ በየዐሥራ አምስት ቀኑ ለኢትዮጵያ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር ሁለት ሁለት ኮፒ ያስገቡበትን ደረሰኝ ለባለሥልጣኑ ማቅረባቸውን አስረድተዋል፡፡ ‹‹ማንነቱ በማይታወቅ የገንዘብ ምንጭ ነው የሚንቀሳቀሰው›› የሚለውን የባለሥልጣኑን ምክንያት ደግሞ “በጥንቆላ ላይ የተመሠረተ መረጃ ነው” ሲሉ አጣጥለውታል፡፡ “ጉዳዩን ይዘን ወደ ፍርድ ቤት እናመራለን” ያሉት አቶ ተመስገን፤ የመጽሔቱ መታገድ ‹‹የአቶ ኀይለማርያም መንግሥት የመለስን ራዕይ እናስቀጥላለን ሲል የነበረውን በተግባር እያረጋገጠ መሆኑን ያመለክታል” ብለዋል፡፡ የአራት ወራት ዕድሜ ያስቆጠረው “አዲስ ታይምስ” መጽሔት ከ35 ሺሕ ኮፒ በላይ እየታተመ በየሁለት ሳምንቱ ይሠራጭ እንደነበር፣ ይህም በአገሪቱ ካሉ መጽሔቶች በኅትመት፣ ብዛትና በተደራሽነት ቀዳሚ እንደሚያደርገው አቶ ተመስገን ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡

በኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን የሕዝብ ግንኙነት ተጠባባቂ ሓላፊ የሆኑት አቶ ወርቅነህ ጣፋ በበኩላቸው፤ ባለሥልጣኑ የእድሳት ክልከላውን ከማድረጉ በፊት ከባለአክሲዮኖቹ ጋር የአድራሻ ቅየራ እና የአክሲዮን ድርሻ ለውጥ ሲደረግ አለማወቃቸው እንዲሁም በቤተ መጻሕፍት ወመዘክር የመጽሔቱ ቅጂዎች እየደረሱ እንዳልሆኑ ተወያይተንባቸው ችግሩ እንዳለ አምነው ተቀብለው ነበር ብለዋል፡፡ የመጽሔቱ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ተመስገን ደሳለኝ፤ የአክስዮኑ 93 በመቶ ድርሻ ባለቤት አገር ውስጥ እንዳልሆኑና ሰባት በመቶ ድርሻ ያላቸው ግለሰብ ብቻ አገር ውስጥ መኖራቸውን በመግለፅ አገር ውስጥ ያሉትን ብቻ አነጋግሮ እዚህ ድምዳሜ ላይ መድረስ እንደማይቻል ተናግረዋል፡፡ አቶ ወርቅነህ የፋይናንስ ምንጩን በተመለከተ ሲናገሩ፤ ‹‹አሁን በግልፅ ይፋ ባናደርግም መረጃው አለን” ብለዋል፡፡ ይህ በዚህ እንዳለ የሕዝብን ሐሳብ ማናወጥ፣ ሕዝቡን በሕገ - መንግሥቱ ላይ ማነሣሣትና የመንግሥትን ስም ማጥፋት የሚሉ ሦስት ክሦች የተመሰረተባቸውና ነሐሴ 17 ቀን 2004 ዓ.ም በቃሊቲ ማረሚያ ቤት ለስድስት ቀናት ከታሰረ በኋላ ክሱ ተቋርጦ በነጻ የተለቀቁት የቀድሞው የፍትሕ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ አቶ ተመስገን ደሳለኝ፤ ከሦስት ወር በኋላ ክሱ በዐቃቤ ሕግ ተንቀሳቅሶ በ50ሺሕ ብር ዋስ መለቀቃቸው ይታወሳል፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት 16ኛ ወንጀል ችሎት ትእዛዝ ታኅሣሥ 27 ቀን 2005 ዓ.ም ቀርበው ተለዋጭ ቀጠሮ የተሰጣቸው የድርጅቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ማስተዋል ብርሃኑ እና የጋዜጣው ዋና አዘጋጅ አቶ ተመስገን ደሳለኝ ትላንት ጥር 23 ቀን 2005 ዓ.ም ቢቀርቡም “መዝገቡን አልመረመርነውም” በሚል ብይኑ ሳይሰማ የቀረ ሲሆን ችሎቱ ለየካቲት 1 ቀን 2005 ዓ.ም እንዲቀርቡ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

የዘፍጥረት ሁለት ትረካዎች ተመሳሳይ አይደሉም? በየዘመኑና በየሃይማኖቱ የሚነገሩ የውኃ ጥፋት ትረካዎችስ?

ወደ ዙፋን የሚወጣ ንጉስ፤ ነባር ስሙ ይቀየራል። ዘውድ የሚደፋው በቀድሞ ስሙ አይደለም- አዲስ ስም ይወጣለታል - ተፈሪ መኮንን፣ አፄ ኃይለሥላሴ እንደተባሉት። ወይም ካሮል ዎይትላ፣ የሮም ካቶሊቅ ጳጳስ የሆኑትም ጆን ፖል በሚል ስያሜ ነው። የአሁኑ ጳጳስ ቤኔዲክት ደግሞ፤ ጆሴፍ ራትዚንገር ነበር ስማቸው። ንግስናም ሆነ ጵጵስና እንደገና እንደመወለድ፤ አልያም የቀድሞው ማንነት ሞቶ በአዲስ መልክ እንደመነሳት ስለሚቆጠር፣ አዲስ ስም ይጎናፀፋሉ። ወደ አዲስ ሃይማኖት የሚገባ ሰው ላይም ተመሳሳይ የስም ለውጥ ይከሰታል። ለምሳሌ የሚጠመቅ ሰው፤ በፈጣሪው ዘንድ ለሁለተኛ ጊዜ እንደተወለደ ወይም ሞቶ እንደተነሳ ይታመን የለ? እናም ሰዎች ሲጠመቁ አዲስ ስም ይወጣላቸዋል። ከ4000 አመት በላይ እድሜ ያስቆጠረው የግብፃዊያኑ ሃይማኖትም እንዲሁ በዳግም ልደትና በጥምቀት፣ በሞትና በትንሳኤ ዙሪያ ያጠነጠነ ነበር - የስም ለውጥ ጭምር። ልደትና ጥምቀት፣ ንግስናና የ30 አመት ህዳሴ፣ ሞትና ትንሳኤ ጥንታዊዎቹ ግብፃዊያን፣ “የሰማያት አምላክ፣ የምድር ንጉስ” እያሉ የሚያመልኩት ሆረስ፣ በአካል ግብፅን እንደገዛ ይነገርለታል። ከሞተ በኋላም ከዙፋን አልወረደም ማለት ይቻላል። ከሱ በኋላ የነገሱ ሁሉ፣ የሆረስ አምሳል እንደሆኑ ይታመንባቸዋልና - የሆረስ ዙፋን ላይ የተቀመጡ አዲስ ሆረስ እንደማለት ነው። ግብፅን የሚገዛ ፈርኦን፣ በምድር ላይ በስጋ የተገለፀ ሆረስ ነው ይባልለታል (በአካል የመጣ አምላክ)። ታዲያ ፈርኦኑ፤ ንጉስ ብቻ ሳይሆን፤ የሃይማኖት መሪም ጭምር መሆኑ ምኑ ይገርማል? የቤተመቅደስ ራስ ነው - High Priest ይሉታል (በብሪቲሽ ሙዚየም የተዘጋጀው Dictionary of Anciet Egypt ገፅ 228)። እንደ እንደ ሊቀ ጳጳስ ነው ማለት ይቻላል። ፈርኦኑ ወይም እንደራሴው በ12 አጃቢና ረዳት ቀሳውስት ጋር የአገሬውን የአይማኖት እምነት ይመራል። እንግዲህ ከአምላክ የተወለደው ሆረስ በግብፅ ምድር በአካል ንጉስ ነበረ ተብሎ ይታመንበት የለ? የሃይማኖትም መሪ ነበር - ንጉስም ሊቀጳጳስም እንደማለት። 12 አጃቢ ቀሳውስት ይኖሩታል። (የአማልክት ጌታ አሞን ወይም ራዕ በአስራ ሁለት አጃቢ አማልክት ተከብቦ እንደሚታየው ማለት ነው።) ከ3500 አመት በፊት በሕንፃዎች ላይ የተቀረፁ ፅሁፎች ናቸው ይህንን የሚመሰክሩት። ANCIENT RECORDS OF EGYPT በሚል ርዕስ University of CH ICAGO ያዘጋጀው መፅሐፍ ውስጥ ተተርጉመው ከቀረቡት ጥንታዊ የግብፅ ሃይማኖታዊ ትረካዎች መካከል ቀንጭቤ ላካፍላችሁ። ፅሁፉ የንግሥና በአልን ይተርካል። በእርግጥ ንግስናው ያልተለመደ ነው። ሴት ነች የምትነግሰው። እንዴት ተደርጎ? እንዴት ነው አንዲት ሴት እንደ ወንድ ሆረስን ሆና በሆረስ መንበር የምትቀመጠው? ከፅሁፎቹ የምናገኘው መልስ ቀላል ነው። ከአምላክ ተወልዳ፣ እንደ ወንድ ሆና ነው የምትነግሰው። ንግስት ተብላ ሳይሆን ንጉስ ተብላ! ለዚያውም እንደ ሌሎቹ ፈርኦኖች የውሸት ፂም መሰል ነገር አገጯ ላይ አንጠልጥላ። ለማንኛውም ፅሁፉ እንዲህ ይላል። Amon-Re enthroned at the right, before twelve gods in two rows at the left. (የሰማያት ዙፋን ላይ ከተቀመጠው የአማልክት ጌታ አሞን-ራዕ ጎን 12ቱን አማልክት የሚያሳይ ስዕል ከፅሁፉ አጠገብ አለ)። ግብፅን ለመግዛት የታጨችው ሴት የፈርኦን ልጅ ብትሆንም፤ አሞንራዕ “የኔ ልጅ ናት” ይላል። ፈርኦኖች ሁሉ አምላክን የሚወክሉ ናቸዋ። የሆነ ሆኖ አሞንራዕ እንዲህ ይላል፤ “ሁሉንም ግዛቶች፣ ሁሉንም አገራት እሰጣታለሁ። መንፈሴ ከውስጧ አለ፣ በረከቴ እሷ ላይ ነው,... ዘውዴ ከሷ ጋር ነው።

ሰሜኑንና ደቡቡን ትገዛለች፣ ሕያዋንን ሁሉ ትመራለች...” አሁን የምትታወቅበት hatshepsut የተሰኘው ስም የሚወጣላትም በዚሁ ጊዜ ነው። ንግስና ማለት እንደገና እንደመወለድ ይቆጠር የለ? እናም፣ ፈጣሪ አምላክ ሃትሸብሱትን በያኔዋ የፈርኦን ሚስት በእናቷ ማህፀን ውስጥ በማስገባት እንድትወለድ ካደረገ በኋላ፤ “ስሟም፤ ክህነመት አሞን ሃትሸብሱት ይሆናል። ግዛቱን ሁሉ በላቀ ጥበብ የምትፈፅም ንግስት ትሆናለች” አለ። አሞንራዕ ደስ ብሎት፣ ለራሷ ለሃትሸብሱት እንዲህ ይላታል - “Glorious part which has come forth from me; king, taking the Two Lands, upon the Horus-throne forever.” “ከኔ የተፈለቅሽ ቅዱስ አካል። ሁለቱን ምድሮች የምትወስጂና በሆረስ ዙፏን ለዘላለም የምትቀመጪ ንጉስ!” ይላታል። ንግስት ሳይሆን ንጉስ አላት - እንደ ሆረስ ነዋ መቆጠር ያለባት። ሆረስ በሌላ አካል የመጣ ያህል ነው። የሷ ንግግሮችም ይህንን የተከተሉ ናቸው። አንደኛ ራሷን ንጉስ ትላለች - ራሷን እንደሆረስ በመቁጠር። ሁለተኛ ራሷን የንጉስ ሚስት ትላለች። ንጉስም የንጉስ ሚስትም ናት። የምድር አባቷን (ቱስሞስን) ኦሲሪስ ብላ ትጠራዋለች፤ እናቷን (አሞስን) ደግሞ ኢሲስ ብላ ትጠራታለች። ኦሲሪስና ኢሲስ ግን የሆረስ ወላጆች ናቸው። በሃትሸብሱት፣ የንግስና በዓል ላይ ሁለት ነገሮች ይፈፀማሉ። እንግዲህ፤ የግብፅ ፈርኦን በ30 አመት ንግስናው እንደሞተ ይቆጠር የለ? “በ30 አመቱ ተጠመቀና እንደገና ተወለደ። በህዳሴ ከሞት ተነሳ” ተብሎ እሱ ራሱ በስልጣኑ ላይ ሊቀጥል ይችላል። አብዛኛውን ጊዜ ግን፤ በንጉሱ አምሳል ልጁ ይነግሳል - በጥምቀት እንደገና ተወለደ ተብሎ፣ ከሞት ተነሳ ተብሎ። ሃትሸብሱትም እንዲሁ በአባቷ ምትክ ዙፋን ላይ እንድትወጣ፤ የምድር አባቷ ዘውድ ሲደፋላት ይታያል - (ስዕል ላይ ስትታይ ወጣት ናት)። በሌላ በኩል ደግሞ፤ በአማልክት ፊት ትጠመቃለች፤ የአማልክት ጌታ አሞንራዕ በላይዋ ላይ ውሃ እያፈሰሰ ያነፃታል (በስዕል ላይ ስትታይ ህፃን ነች። መጠመቅና ንግስና እንደገነና ነፅቶ መወለድን ያመለክታል ብለው ስለሚያምኑ)። በጥምቀቱ ላይ፤ የአሞን ራዕ 12 አጃቢ መላእክት በአንድነት ይናገራሉ፤ “ከታችኛውና ለላይኛው ግብፅ ታላቅ የንጉስ ክብር፣ ከነፍስሽ ጋር ነፅተሻል (ነፅተሃል)” ይላሉ። “ወርቃማ ሆረስ... የላይኛውና የታችኛው ግብፅ ንጉስ” የሚል ተጨማሪ ስም ይወጣላታል። የወንድ ንጉሥ ልብስ አድርጋ ንግስናዋ ሲታወጅም በስዕል ይታያል። ንጉሥ ብቻ ሳትሆን የአምላክ ተወካይም ነችና፤ እንደ ሊቀ ጰጳስ ነች - እንደ ሆረስ (12 ቀሳውስት የሚያጅቡት ሊቀ ቀሳውስት)።

ANCIENT RECORDS OF EGYPT V.2 ከገፅ 202 - 292። እንግዲህ፤ የአምላክ ልጅነትና ንግስና፣ ውልደትና የሰላሳ አመት ጥምቀት፣ የሞትና የትንሳኤ ... በጥንታዊያኑ የግብፅ ሃይማኖት ውስጥ ምን ያህል ቦታ እንዳለው ከዚህ ትረካ ማየት ይቻላል። የሆረስ ታሪክ ከኢየሱስ፣ ከሚትራ፣ ከክሪሽና፣ ከዲኖስየስ ጋር ይመሳሰላል የሚባልበት አንዱ ምክንያትም ከእንደዚህ አይነት ትረካዎች የተነሳ ነው። በእርግጥ፤ “ምንም ተመሳሳይነት የለም” ብሎ መሸምጠጥም ይቻላል። ነገር ግን፤ የልዩነቶች መኖር ተመሳሳይነትን አያስቀርም። ለልዩነት ለልዩነትማ፤ በዘፍጥረት ምዕራፍ አንድ እና ሁለት መካከልም በርካታ ልዩነት አለ። የዘፍጥረት ሁለት ትረካዎች አንደኛው ትረካ፡ ዘፍጥረት ምዕራፍ 1 ላይ፤ መጀመሪያ ቀንና ሌሊት፣ በሁለተኛው ቀን ሰማይን፣ በሶስተኛው ቀን ምድርና ባህርን እንዲሁም እፀዋትን፣ በአራተኛው ቀን ፀሐይ፣ ጨረቃና ኮኮቦችን ፈጠረ። በአምስተኛው ቀን፤ ከውኃ የባሕር እንሰሳትንና በራሪ አእዋፋትን ፈጠረ። በስድስተኛው ቀን ከምድርም አራዊትን ፈጠረ። በመጨረሻም ሰውን በእግዚአብሔር መልክ ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው። እናም ባረካቸው፤ “... የባሕርን ዓሦችና የሰማይን ወፎች በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ግዙአቸው። ...እነሆ መብል ይሆናችሁ ዘንድ በምድር ፊት ሁሉ ላይ ዘሩ በእርሱ ያለውን ሐመልማል ሁሉ፥ የዛፍን ፍሬ የሚያፈራውንና ዘር ያለውንም ዛፍ ሁሉ ሰጠኋችሁ። ለምድርም አራዊት ሁሉ፥ ለሰማይም ወፎች ሁሉ፥ ሕያው ነፍስ ላላቸው ለምድር ተንቀሳቃሾችም ሁሉ የሚበቅለው ሐመልማል ሁሉ መብል ይሁንላቸው” አለ። “እንዲሁም ሆነ። እግዚአብሔርም ያደረገውን ሁሉ አየ፥ እነሆም እጅግ መልካም ነበረ”... በሰባተኛው ቀን እረፍት ሆነ። ሁለተኛው ትረካ፡ በምዕራፍ 2 ላይ የምናገኘው ታሪክስ ምን ይመስላል? እስካሁን እግዚአብሄር እንዲህ አለ፣ እንዲህ አደረገ እያለ ሲተርክ የነበረው “ዘፍጥረት” ምዕራፍ 2 አንቀፅ 4 “እግዚአብሔር አምላክ...” የሚል አጠራር መጠቀም ይጀምራል። እናም ምድርና ሰማይ የተፈጠሩ ጊዜ፣ አንዳችው ቁጥቃጦና ቡቃያ በምድር ላይ እንዳልነበረ በመግለፅ የፍጥረት ትረካውን በአዲስ መልክ መልሶ ያቀርባል። የምድር ቡቃያ ያልነበረው ስላልዘነበ መሆኑን፤ የሚሰራበት ሰውም እንዳልነበረ ይገልፃል። በቀድሞው ትረካ ሰው (ወንድና ሴት) በእግዚአብሔር አምሳያ እንደተፈጠሩ ቢጠቀስም፤ አሁን ግን አዳምን ብቻ ከአፈር ይፈጥረዋል። “እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ከምድር አፈር አበጀው፤ በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት” ይላል። በኋላም “አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ” ይለዋል። ታዲያ ይሄ የእግዚአብሔር አምሳል ነው? የሆነ ሆኖ፤ አዳም ከተፈጠረ በኋላ በምር ላይ እፅዋት ያለበት አካባቢ (ገነት) ይፈጠርና አዳምን እዚያ ወስዶ ያስቀምጠዋል። ከሰው በፊት እፀዋትና እንሰሳት አልተፈጠሩም እንዴ? የመጀመሪያው ትረካ ላይ... አዎ። እና ደግሞ፤ የሁሉም ነገር ገዢ ሆኗል፤ ከቅጠሉም፣ ከፍሬውም፣ ከእንስሳውም ያሻውን መጠቀምና መብላት ትችላለህ የሚል ስልጣን ተሰጥቶታል። ገዢ ሆኗል። ትዕዛዝ አልተጫነበትም። በሁለተኛው ትረካ ግን በቅድሚያ ሰው ተፈጠረና፣ ከዚያ እፀዋት መጣ። እናም ትዕዛዝ ተከተለ። “እግዚአብሔር አምላክም ሰውን እንዲህ ብሎ አዘዘው። ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና”። ከዚያ፤ “እግዚአብሔር አምላክም የምድር አራዊትንና የሰማይ ወፎችን ሁሉ ከመሬት አደረገ” ይላል። በምዕራፍ 1 ላይ፤ እፀዋት ብቻ ሳይሆኑ፤ አራዊትን ከምድር፤ አእዋፍና የባሕር እንስሳትም ከውኃ የተፈጠሩት ከሰው በፊት ነው። በምዕራፍ 2 ትረካ ላይ ግን፤ ሰው በቅድሚያ መፈጠሩን እናነባለን። አእዋፋትም ከውኃ ሳይሆን ከመሬት መፈጠራቸውን ይነግረናል። ሁለተኛው ትረካ ላይ ያለ ሴት የተፈጠረው አዳም፣ ረዳት ያሻዋል ተባለና በተኛበት አንድ የጎድን አጥንቱ ተወስዶ ሴት ተሰራች። (ተፈጠረች፤ ተወለደች)። ከአጥንቴና ከስጋዬ የተገኘች ይላታት። ከዚያ ሚስቱ ትሆናለች። ... ገና ሚስቱ አልሆነችም። እንዲያውም፤ ወንድና ሴት መሆናቸው ግድ አልሰጣቸውም። አላወቁም። አይናቸው አልተከፈተም ነበር። ተንኮለኛው እባብ ነው፤ አይናቸው እንዲከፈት መዘዝ የሆነው። በገነት መሃል ካለው የዛፍ ፍሬ (መልካሙንና ክፉውን ለመለየት ከሚያስችለው ፍሬ) የበላ ይሞታል የሚል ትዕዛዝ ቢኖርም፤ እባብ ግን “አትሞቱም” ብሎ ለሴቷ ለሄዋን ይነግራታል። እንዳትበሉ የተከለከላችሁት፤ “በበላችሁ ቀን ዓይኖቻችሁ እንደሚከፈቱ፣ እንደ አማልክትም መልካምንና ክፉን የምታውቁ እንደምትሆኑ እግዚአብሔር ስለሚያውቅ ነው...” ብሎ ያግባባታል። በእርግጥ እባቡ እንዳለውም፤ ፍሬውን ሲበሉ፤ አልሞቱም፤ አይኖቻቸው ተከፈቱ፤ ወንድና ሴት መሆናቸውንም አወቁ። ደግሞም እንደ አማልክት ትሆናላችሁ ብሏቸዋልኮ። በእርግጥሞ ሆነዋል። ምዕራፍ ሁለት ማጠቃለያ እንዲህ ይላል። ... እግዚአብሔር አምላክም፤ እነሆ አዳም መልካምንና ክፉን ለማወቅ ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ አለ። አሁንም እጁን እንዳይዘረጋ፥ ከሕይወት ዛፍ ወስዶ እንዳይበላ፥ ለዘላለምም ሕያው ሆኖ እንዳይኖር፤ እግዚአብሔር አምላክ ከዔድን ገነት አስወጣው፥ የተገኘባትን መሬት ያርስ ዘንድ። በመጀመሪያው ምዕራፍ አተራረክ፤ አዳምና ሄዋን በአምላክ አምሳያ ነው ህልውና ያገኙት። በምዕራፍ 2 አተራረክ ግን፤ ምኑንም ምኑንም የማያዋቁ አዳምና ሄዋን፤ የተከለከለ የዛፍ ፍሬ ከበሉ በኋ ነው የአምላክ አምሳያ የሆኑት። ግን፤ የዘላለማዊነትን ዛፍ እንዳይበሉ ከገነት ተባረሩ። እንግዲህ፤ ከዚህ በኋላ ነው ባልና ሚስት የሆኑት። የኔ ጥያቄ የምዕራፍ 1 እና የምዕራፍ 2 ትረካዎች በርካታ ልዩነቶች ቢኖሯቸውም፤ ተመሳሳይነታቸው የጎላ አይደለም ወይ የሚል ነው። የቅደም ተከተልና የዝርዝር ነጥቦች ልዩነት ቢኖርም፤ ሁለቱ ትረካዎች መሰረታዊ ልዩነት የላቸውም ማለት ይቻላል። በአጭሩ፤ ነገሮቹን በሙሉ እግዚአብሔር እንዳሻው አድርጎ ፈጠራቸው የሚል ነው የሁለቱ ትረካዎች መሰረታዊ ሃሳብ። በዚያ ላይ፤ የተፈጠሩት ነገሮች ያው ተመሳሳይ ናቸው። ሰማይ፣ ምድርና ባሕር፣ እፀዋትና አራዊት፣ እና ሰው! በእርግጥ፤ የ3200 አመት እድሜ አስቆጥሯል በሚባለው ጥንታዊ የፔርሺያ የሃይማኖት መፅሐፍም ስለ ፍጥረት ይተርካል። አምላክ ሁሉን ነገር በ6 ወቅቶች እንደፈጠራቸው የሚገልፀው አቬስታ የተሰኘው ጥንታዊ ሃይማኖታዊ መፅሐፍ፤ በቅድሚ ሰማያት፣ ቀጥሎ ባሕሮች፣ ከዚያ መሬት፣ ከዚያ እፀዋት፣ ከዚያ እንሰሳት፣ በስድስተኛውም ወቅት ሰው እንደተፈጠረ ይተርካል። ... BIBLE MYTHS AND THEIR PARALLELS IN OTHER RELIGIONS (ገፅ 7)። ታዲያ ይሄኛው ትረካና የዘፍጥረት ትረካስ አይመሳሰልም? የኖህ ታሪኮች በየአገሩና በየሃይማኖቱ የኖህ ታሪክን ጨምሮ፣ የ”ባይብል” የመጀመሪያዎቹ አምስት መጻሕፍት፣ ከ2500 እስከ 3000 አመት እድሜ ካላቸው ሰነዶች የተዋቀሩ እንደሆነ የሚናገሩት ተመራማሪዎች፤ ቢያንስ የሁለት ሃይማኖታዊ ቡድኖች የተውጣጣ እንደሆነ ይናገራሉ። የሁለቱ ቡድኖች ትረካ በ”ዘፍጥረት” ተደራርቦ እንደቀረበው ሁሉ፤ በኖህ ታሪክም ላይ ሁለት ትረካዎች ይደጋገማሉ። መቼም የኖህ ታሪክ ቢያንስ በከፊል ምሳሌያዊ አነጋገር መሆኑ አያጠራጥርም። መጽሐፉ እንደሚለው፤ ኖህ ከአዳም በ10ኛ ትውልድ ነው። በ10 ትውልድ እንዴት ነው፤ አለም በሰው ልጆች ቆሻሻና ክፋት ተሞላች ሊባል የሚችለው? እንዲያ ከአዳም ጀምሮ ሁሉም በሕይወት ቢኖሩ እንኳ ቁጥራቸው አንድ ሚሊዮን አይደርስም። እንደ ኖህ ሶስት ልጆችን ወይም እንደ አዳም 6 ልጆችን የሚወልዱ ከሆነ ደግሞ በምድር ላይ የሰዎች ቁጥር በጣም ትንሽ መሆን አለበት። የሆነ ሆኖ ፈጣሪ በጎርፍ ከኖህና ከልጆቹ በቀር ሰዎችን ሊያጠፋ ስለወሰነ፤ ኖህ መርከብ እንዲሰራ ታዘዘ። በአንደኛው ትረካ፡ ኖህ ከምድር ተንቀሳቃሽ ፍጥረታት ሁሉ ሁለት ሁለት ከሴትና ከወንድ ወደ መርከብ እንዲያስገባ ተነገረው ይላል ዘፍጥረት 6፡20። ከእያንዳንዱ የእንሰሳ አይነት አንድ ወንድ አንድ ሴት ለምሳሌ አንድ በሬና አንድ ላም እንደማለት ይመስላል። ሁለት በሬ፣ ሁለት ላም የሚል ትርጉምም ሊኖረው ይችላል። ሁለተኛው ትረካ፡ ንፁሕ ከሆኑት እንሰሳትና አእዋፋት ሰባት ወንድ ሰባት ሴት፤ ንፁሕ ካልሆኑት ደግሞ ሁለት ሁለት ወደ መርከቡ ውስጥ እንዲያስገባ እንደታዘዘ ይገልፃል ዘፍጥረት 7፡2-3። ለምሳሌ ሰባት በሬ ሰባት ላም እንደማለት ነው። ፈጣሪ ለኖህ የሰጠው ትዕዛዝ የትኛውም ቢሆን፤ በሰባት ቀን ውስጥ የጥፋት ውኃው እንደሚጀምር ተነግሮታል። ዝናቡና ጎርፉ ለአርባ ቀንና ሌሊት አያቋርጥም ተብሏል። ኖህ፣ በታዘዘው መሰረት መርከብ ሰርቶ፣ በታዘዘው መሰረት እሱና ቤተሰቡ፤ እንዲሁም ከእንሰሳት ዘር ሁሉ ሰብስቦ አስገባ። ግን ሰባት ሰባት እየሆነ የገባ የእንሰሳ አይነት እንደሌለ ይገልፃል።

በመፅሐፉ መሰረት አንደኛው ትረካ ነው ተግባራዊ የሆነው። አንደኛ ትረካ፡ ከምድር ተንቀሳቃሽ እንስሳት ሁሉ፤ ከወፍና ከነፍሳት ሁሉ፤ ንፁሕ የሆኑም ያልሆኑትም እንሰሳት፤ ሁለት ሁለት ሴት እና ወንድ እየሆኑ ወደ መርከብ እንደገቡ ይገልፃል - ዘፍጥረት 7፡8-9። ከእያንዳንዱ የእንሰሳ አይነት አራት ማለት ነው? ወይስ ሁለት? ለነገሩ ሁለት ብቻ ቢሆን እንኳ ቀላል እንዳይመስላችሁ። በምድር ላይ 5 ሚሊዮን ያህል የነፍሳት አይነቶች እንዳሉ ይገመታል - ዝንብ፣ ንብ፣ በረሮ። ከእያንዳንዱ አይነት ሁለት ሁለት እየተመረጠ በአጠቃላይ 10 ሚሊዮን ያህል ነፍሳት ወደ መርከቡ ይገባሉ ማለት ነው። በባህር ወይም ውሃ ውስጥ የሚኖሩትን ትተን፣ ጥቃቅኖቹን ነፍሳትም ሳይቆጠሩ፤ ወደ 20 ሺ ገደማ የተለያዩ የምድር እንሰሳት አሉ - እንሽላሊት፣ ዝሆን፣ ግመል፣ ጥንቸል፣ ጊንጥ፣ አሞራ... ወዘተ። ሁለት ሁለት እየሆኑ በአጠቃላይ ወደ 40 ሺ እንሰሳት ወደ መርከቧ ይገባሉ። የእግር ኳስ ሜዳ በማታክል መርከብ ውስጥ ማለት ነው። በዚያ ላይ የምግብና የውሃ ስንቅ መያዝ እንደሚገባው ታዟል። የኖህ ቤተሰቦችና እንሰሳቱ ሁሉ ከመርከቧ የሚወጡት ከአስራ ሁለት ወራት በኋላ ነዋ። ለ8ቱ የኖህ ቤተሰቦች፣ በሺህ ለሚቆጠሩ እንሰሳት፤ በሚሊዮን ለሚቆጠር ነፍሳት... የአንድ አመት ቀለብና ውሃ ብዙ ነው። እንግዲህ፤ የነገሩን አስቸጋሪነት ሲታይ ነው፤ የኖህ ታሪክ በከፊል ምሳሌያዊ ትረካ መሆን አለበት የሚባለው። ለማንኛውም የጥፋት ውኃ ከ5 ወራት በኋላ መጉደል እንደጀመረ፣ የኖህ መርከብ በአራራት ተራሮች ላይ እንደተቀመጠች፣ በ10ኛው ወር የተራሮች ጫፍ እንደታየ የሚተርከው ዘፍጥረት፤ ኖር መስኮት ከፍቶ ቁራ እና እርግብ እንደሰደደ ያወሳል። እርግቧ የምታርፍበት ቦታ አጥታ ተመለሰች፤ ከሰባት ቀን በኋላ ሲልካት በአፏ የወይራ ቅጠል ይዛ መጣች። አዲስ የበቀለ ይሁን ለአስር ወራት በጎርፍ ተቀብሮ የነበረ ወይራ ይሁን ባይታወቅም፤ ቅጠሉ ለምለም ነው። እንደገና ከሰባት ቀን በኋላ ለሶስተኛ ጊዜ እርግባን ሰደዳት፤ ተመልሳ አልመጣችም። ከ10 ወር ተኩል በኋላ የመርከቧ ክዳን ተከፈተ። ኖህ ከመርከቡ የወረደው ደግሞ አስራ ሁለት ወር ከደፈነው በኋላ ነው። ለእግዚአብሔርም መስዋዕት አቀረበ።

የሰው ዘር በሙሉ ከኖር ሶስት ልጆች ከሴም፣ ከካም እና ከያፌት ትውልድ የሚመዘዝ ሆነ ማለት ነው። የግሪኮቹ ኖህ ዱካልዮን ይባላል። አምላከ አማልክት ዙውስ፤ በሰው ልጆች የክፋት መንገድ ተቆጥቶ፤ የውኃ ጥፋት አዘዘባቸው። ለዘጠኝ ቀንና ሌሊት ዶፍ ዝናብ ለቀቀባቸው። ዱካልዮን ግን የአማልክቱን ሕግ የሚያከብርና የእውነትን መንገድ (በጽድቅ መንገድ) ይከተል ነበር። በዚህም ምክንያት የሰው ልጅን ከሚያጠፋ የውኃ መጥለቅለቅ እንዲድን ከአምላክ ተነግሮት መርከብ ሰርቷል። ውኃው አለምን እያጥለቀለቀ ሰው እና እንስሳን ሁሉ እየገደለ ሸለቆውን ብቻ ሳይሆን ተራሮችንም ይውጣል። ኩካልዮን እና ሚስቱ ግን መርከባቸው ውስጥ ናቸው። ውኃው መርከቧን እያንሳፈፈ ፓርናሰስ ተራራ ላይ አሳረፋት። በዚህ መንገድ ከሚስቱ ጋር ከጥፋት ውኃ ያመለጠው ዱካልዮን፤ ለአምላክ ዙውስ መስዋዕት አቀረበ። ሦስት ልጆችንም ወለደ። የሰው ዘርም ከሶስቱም ልጆች የሚመዘዝ ነው። በህንድ የሰንስክሪት ሃይማኖታዊ ፅሁፎችም ስለ ውኃ ጥፋት ይተርካሉ። ምድርና ሰማይ ከተፈጠሩ ከብዙ ዘመናት በኋላ በሰዎች ክፉ ተግባር የተነሳ ፈጣሪ በውኃ ሊያጥለቀልቃት ቢወስንም፤ አንድ በፅድቅ መንገድ የሚኖር ነበር - ሳትያራታ የሚባል። ፈጣሪ አምላክም ወደ ሳትያራታ መጥቶ፣ በ7 ቀን ውስጥ የጥፋት ውኃ እንደሚመጣ ነገረው። ግን ላንተ መርከብ ሰርቼ እሰጥሃለሁ። እፀዋትን ሁሉ፣ ከእንሰሳትም ሴት እና ወንድ ጥንዶችን ሰብስበህ ወደ መርከባ ግባ። ከውሃ ጥፋትም ትድናለህ አለው። የባሕር ምንጮች ተከፈቱ፤ የዝናፍ ዶፍ ወረደ። ምድር ተጥለቀለች። ሳትያራታ እና በመርከቧ ውስጥ የገቡ እፀዋትና እንሰሳት ግን ከጥፋት ዳኑ። ዳትያራታም ለአምላክ መስዋእት አቀረበ። BIBLE MYTHS AND THEIR PARALLELS IN OTHER RELIGIONS (ገፅ 24 - 25)። በእርግጥ የሰንስክሪት ፅሁፎች እድሜ 2400 ገደማ እንደሆነ ምሁራን ይገልፃሉ። የባቢሎናዊያኑ ትረካ ግን የ4000 አመት እድሜ አለው። ከ4000 አመት በፊት የተፃፈው የአትናፒሽቲም ታሪክ ከኖህ ጋር እንደሚመሳሰል ለብዙዎች አከራካሪ አይደለም። የዛሬዋ ኢራቅ የያኔዋ ባቢሎን አለምን ካጥለቀለቀው የጎርፍ ጥፋት እንደ ኖህ የተረፈው ሰው አትናፒሽቲም ይባላል። ስለጎርፉ እና ስለ አትናፒሽቲም ታሪክ ተፅፎ የሚገኘው፤ ከጊልጋሜሽ ገድል ጋር ነው። የጊልጋሜሽ ገድል Gilgamesh Epic በመባል የሚታወቀውና በ12 ሸክላዎች ላይ ተፅፎ የተገኘው ትረካ፤ የንጉስ ጊልጋሜሽን ጀግንነት ይዘረዝራል። ከዚሁ ጋር ግን፤ በጥንት ዘመን የሰው ልጅን ከምድረ ገፅ የሚያጠፋ የውኃ መዓት ደርሶ እንደነበር ይተርካል። በእብራውያኑ የኖህ ታሪክ፤ የውኃ ጥፋት የመጣው ከአዳም በ10ኛው ትውልድ በኖህ ዘመን እንደሆነ ይገልፃል። የባቢሎናውያኑ ትረካ ደግሞ፤ በ10ኛው ስርወመንግስት የጥፋት ውኃ አጋጥሞ፤ ኡትናቢሽቲም ብቻ እንደተረፈ ይገልፃል። አምላክ ባዘዘው መሰረት መርከብ ሰርቶ ከሁሉም የእንሰሳት አይነቶችም ሰብስቦ መርከቡ ውስጥ ገባ። በስድስት ቀን ዶፍ ዝናብ አለም ተጥለቀለቀች። መርከቧ ተንሳፍፋ ናሲር ተራራ ላይ አረፈች። በመጨረሻ ዝናቡ ሲቆም፤ ውሃው መጉደሉና አለመጉደሉን ለማወቅ እርግብ ሰደደ። በመጨረሻም ከነሚስቱ ከመርከቧ ወርዶ ለአምላክ መስዋእት አቀረበ። THE EPIC OF GILGAMESH፣ PENGUIN BOOKS 1999፣ ከገፅ 88 -100

 የጎፋ ቅ/ገብርኤል ምእመናን በደብሩ አስተዳዳሪ ተማረዋል

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስትያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ‹‹መሠረተቢስ መረጃዎችን በማስተላለፍ ሕዝቡን ለማደናገር ይሠራሉ›› ባላቸው የሚዲያ ተቋማት ላይ ክስ መመሥረቱን አስታወቀ። በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ በወጣው ደብዳቤ እንደተገለጸው÷ ክሥ የተመሠረተባቸው አራቱ የሚዲያ ተቋማት÷ የኛ ፕሬስ ጋዜጣ፣ አርሒቡ፣ ሊያ እና ሎሚ የተባሉ መጽሔቶት ናቸው፡፡
የቅዱስ ፓትርያሪኩን ዜና ዕረፍት ተከትሎ ያለውን የሽግግር ወቅት በሰላማዊ መንገድ ለማከናወን ቅ/ሲኖዶስ በአንድነትና በመደማመጥ መንፈስ በተለያዩ ጊዜያት ጉባኤያትን በማድረግ፣በውጭም በውስጥም ያለውን ተጨባጭ ኹኔታ በመዳሰስና በሐቅ ላይ በመመርኮዝ የስድስተኛውን ፓትርያርክ ምርጫ ለማካሄድ ተግባራዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ መኾኑን መምሪያው ገልጾ÷ ‹‹አንዳንድ የነጻው ፕሬስ አባላት ሓላፊነት በጎደለው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ የሚመራውን የቅ/ሲኖዶስ ጉባኤ ውሎ በማብጠልጠልና በመተቸት የሚያወጧቸው ዘገባዎች በእጅጉ አሳዛኝና ቤተ ክርስቲያኒቱን ኾነ ብለው ለመበጥበጥ የተነሡ ያስመስላል›› ብሏል፡፡
በሕዝብ ግንኙነት መምሪያው ደብዳቤ እንደተመለከተው፣ በስም የተጠቀሱት ፕሬሶች በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትም ኾነ በሚመለከታቸው አካላት ማብራሪያና መግለጫ ያልተሰጠበትን ዜና ‹‹ከልዩ ልዩ የመረጃ መረቦች አግኝተናል›› በሚል ሽፋን ጽፈዋል፡፡ መምሪያው ‹‹በአባቶች መካከል ጠብና ችግር አለ ብሎ አንባቢው እንዲያምን ለማድረግ የሚጻፉ ናቸው›› ያላቸው እኒህ ጽሑፎች፣‹‹መሠረተቢስ አሉባልታዎች ብቻ ሳይሆኑ ቤተ ክርስቲያኒቱን የማፈራረስና ቅ/ሲኖዶሱን የመበታተን ዓላማ ያነገቡ ናቸው፡፡››
በመኾኑም በስም በተጠቀሱት አራት የፕሬስ ውጤቶች ላይ ቤተ ክርስቲያኒቱ ክሥ መመሥረቷንና ሕግና ሥርዐቱ በሚፈቅደው መሠረት ጉዳዩን በመከታተል የሕግ እርምት እንዲወሰድ በመንቀሳቀስ ላይ መኾኗ ተመልክቷል። ትክክለኛ መረጃን ለሕዝቡ ለማድረስ የሚመለከታቸውን አካላት በማነጋገር እውነተኛውን ዜና የሚያስተላልፉ የግል ሚዲያ ተቋማትን ቤተ ክርስቲያኒቱ እንደምታደንቅና እንደምታመሰግን በደብዳቤው የገለጸው መምሪያው፣ በሚመለከተው የቤተ ክርስቲያኒቱ አካል መግለጫ ያልተሰጠባቸው ዘገባዎች ሁሉ ‹‹የሽግግር ወቅቱ በሰላማዊ መንገድ እንዳይከናወን የሚጥሩ ሰዎች የሚያናፍሱት የሐሰት ወሬ›› መኾኑን ሕዝቡ እንዲያውቀው ጠይቋል፡፡
በሌላ በኩል በአሁኑ ወቅት በቤተ ክህነቱ የተለያዩ ደረጃዎች የሚታዩ አስተዳደራዊ ችግሮች እየተባባሱ መኾናቸው፣ በየጊዜው ለአዲስ አድማስ ዝግጅት ክፍል እየደረሱ ያሉ የካህናትና ምእመናን አቤቱታዎች ያስረዳሉ፡፡ በተደጋጋሚ የዘገብነው በሰሜን ወሎ ሀ/ስብከት የቅ/ላሊበላ ደብረ ሮሃ ገዳም አስተዳደራዊ ችግር ዋነኛ ማሳያ ሲሆን በአስተዳደሩ ላይ ሲነሣ የቆየውና የከተማውን አስተዳደር ጨምሮ በመንግሥትና በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ከፍተኛ አካላት ዘንድ ሳይቀር በሚገባ የሚታወቀው የካህናቱና ምእመናኑ ጥያቄ በተለያዩ አጋጣሚዎች መመሪያ እንደተሰጠበት ቢነገርም እስከ አሁን በተጨባጭ ምላሽ እንዳላገኘ ነው የተዘገበው፡፡
ለመልካም አስተዳደር እንዲያመች በሚል በጥቅምቱ የቅ/ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መደበኛ ስብሰባ ውሳኔ÷ ለአራት በተከፈለው በአዲስ አበባ አህጉረ ስብከት ሥር በሚገኙ አንዳንድ አድባራትም ከሙስናና ብልሹ አሠራር ጋራ ተያይዘው በካህናቱና ምእመናኑ የሚነሡ በርካታ ጥያቄዎች እንዳሉ ለዝግጅት ክፍሉ የሚደርሱ መረጃዎች ያስረዳሉ፡፡ በደቡብ አዲስ አበባ ሀ/ስብከት የጎፋ መካነ ሕያዋን ቅ/ገብርኤል ካቴድራል÷ በካቴድራሉ አስተዳዳሪ ከእርሳቸውም ጋር በጸሐፊነት፣ በሒሳብ ሹምነት እና በገንዘብ ያዥነት በሚሠሩ የአስተዳደሩ ሠራተኞች ላይ ካለፈው ዓመት መጨረሻ ጀምሮ የሚነሡትና ከሀ/ስብከቱ ጽ/ቤት ባሻገር የመንበረ ፓትርያሪክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቱ ጭምር እንደሚያውቀው የተነገረው አንድ የችግሩ አብነት ነው፡፡
በካቴድራሉ ሰንበት ት/ቤት እንደሚያገለግሉ የገለጹት ምእመናኑ ለዝግጅት ክፍላችን በሲዲና በሰነድ ያደረሷቸው መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፣ በክብረ በዓላትና በተለያዩ ጊዜያት ደብሩ በመባዕና በስእለት ለሚያገኘው ገንዘብና ንብረት ቆጠራ የሚካሄደው ግልጽነትንና ተጠያቂነትን የሚያሰፍነውን መመሪያ በመከተል ሳይሆን በአስተዳዳሪው ቀራቢዎች ነው፤የካቴድራሉ ገንዘብና ንብረት በትክክለኛ ሞዴላ ሞዴሎች ገቢ አይደረጉም፡፡ ከካቴድራሉ የንዋያተ ቅድሳት መሸጫና ሱቁ በተጓዳኝ ከሚሠራቸው የጨረታና የጉዞ አገልግሎቶች የሚሰበሰበው ገቢ በአግባቡ አይታወቅም፡፡
ሁለተኛውን ፓትርያሪክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስን ለመዘከር በተሠራው የአንደኛና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ከሚማሩ ተማሪዎች ክፍያ በሁለት ደረሰኞች የሚሰበሰብ ሲኾን አንዱ ደረሰኝ በካቴድራሉ ሰበካ ጉባኤም ሆነ በሀ/ስብከቱ አይታወቅም፡፡ ከፍለው ለመማር አቅም የሌላቸውን ተማሪዎች በበጎ አድራጊዎች ስፖንሰርሽፕ ለመደገፍ አስተዳደሩ የሚከተለው አሠራር ለምዝበራ የተጋለጠ በመኾኑ በችግረኛ ተማሪዎች ስም እየተነገደ ነው፡፡
በካቴድራሉ ደጃፍ መንግሥት በሰጠው ፈቃድ በካቴድራሉ ወጪ የሚሠራው የዝክረ ቴዎፍሎስ ዐደባባይ ሦስተኛ ዓመቱን ቢያስቆጥርም በየጊዜው ኾነ ተብሎ ዲዛይኑንና ጥራቱ ጠብቆ እንዳይሠራ እየተደረገ ግንባታው እየተጓተተ ነው፡፡ በግንባታው ሰበብ የሚገዙ የግንባታ ማቴሪያሎችና በቃል ኪዳን ሰነድ የተሰበሰበው ገንዘብ የግለሰቦች መኖሪያ ቤት መሥሪያና የግል ኑሮን ማበልጸጊያ እንደኾነ በምሬት የሚናገሩት ምእመናኑ÷ በቀድሞው አስተዳደር በአግባቡ ተጠብቆ የቆየው የካቴድራሉ ሕንጻ ቤተ መቅደስና የቅጽረ ቤተ ክርስቲያኑ ገጽታ በወቅቱ አስተዳደር ትኩረት የተነፈገው በመኾኑ በከፍተኛ ደረጃ መጎሳቆሉን፣ በአንጻሩ በካቴድራሉ ይዞታዎች በቤተ ክርስቲያን ቅጽር መገኘት የማይገባቸው ግለሰቦች ከአስተዳደሩ ጋራ በፈጠሩት የጥቅም ትስስር ለቤተ ክርስቲያን ቅድስናና ክብር ተቃራኒ የኾኑ ንግዳዊ ሥራዎችን (የከሰል፣ የአጠና ሽያጭና የአሳማ ርባታ) እንደሚያካሂዱ የሚናገሩት በከፍተኛ የሐዘን ስሜት ተውጠው ነው፡፡
ምእመናኑ በሰነድና በቃል ማብራሪያ አስደግፈው በካቴድራሉ አስተዳደር ላይ የሚያሰሟቸው አቤቱታዎች÷ የሰበካ ጉባኤ ቃለ ዐዋዲን፣ የቀኖና ቤተ ክርስቲያንንና የክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር ጥሰትን የተመለከቱ ተጨማሪ አቤቱታዎችን ያካተተ ሲሆን ካለፈው ዓመት ሐምሌ ወር ጀምሮ ለመፍትሔው እንቅስቃሴ ሲደረግባቸው መቆየቱ ተገልጧል፡፡ አቤቱታዎቹ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በሠየመው አጥኚ ኮሚቴ በሚጣሩበት ወቅት የካቴድራሉ አስተዳደር ያመነባቸው ከመኾኑም በላይ ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ ለአምስት ዓመታት በአስተዳዳሪነት የቆዩት ቆሞስ አባ ኀይለ መለኰት ይኄይስ ከሓላፊነት ተነሥተው ለካቴድራሉ መንፈሳዊ አገልግሎትና የልማት አቅም በሚመጥን አለቃ እንዲተኩ ተወስኖ እንደነበር ምእመናኑ ያስታውሳሉ፡፡
ውሳኔውን በአግባቡ ተፈጻሚ በማድረግ መፍትሔ እንዲሰጣቸው በጥቅምት መጨረሻና በጥር መጀመሪያ ላይ ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጽ/ቤትና ለቅ/ሲኖዶስ ጽ/ቤት ጥያቄዎቻቸውን በተደራጀ አኳኋንና በሰላማዊ መንገድ እያቀረቡ እንደሚገኙ ምእመናኑ ገልጸው÷ የካቴድራሉ አስተዳደር ግን ይባስ ብሎ ‹‹አቤቱታ አቅራቢዎችን ተባብረዋል›› በሚል ዐሥር የካቴድራሉን ካህናት ከደመወዝና ከሥራ ማገዱን፣በካቴድራሉ ይዞታ ከሚገኘው መኖሪያ ቤቶቻቸውም እንዲለቁ ማዘዙን፣ ካቴድራሉ የሚገባውን ብቁ አስተዳደር እንዲያገኝ በሥርዐት የሚንቀሳቀሰውን የሰንበት ት/ቤት አመራርም በዐመፀኝነትና በፖለቲከኝነት በመወንጀል ከፍተኛ ጫና እየፈጠሩበት መኾኑን አስረድተዋል፡፡ በሓላፊነት ላይ የሚገኙት የካቴድራሉ አስተዳዳሪ ከሥልጣናቸው መነሣት ብቻ ሳይሆን የሕዝብን ሀብት ለብክነትና ለምዝበራ በመዳረጋቸው በሕግ መጠየቅ እንዳለባቸው የሚከራከሩት አቤቱታ አቅራቢዎቹ፣ በሕግ አገባብ ለሚመለከተው የፍትሕ አካል አስፈላጊውን ማስረጃ ለማቅረብ ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውን አስታውቀዋል፡፡


አሳ ሁልጊዜ በመረብ ብቻ አይጠመድም፡፡ የመኖሪያ ቤት ግዢ የብድር ፕሮግራሙ እንዲህ ያለ አሳዛኝ ውጤት በማስመዝገብ ሲከሸፍ፣ ብዙዎቹ ቤተእስራኤሎችና እነሱን ለመርዳት ተብለው የተቋቋሙ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የእስራኤል መንግስት ቤተእስራእሎችን ለማዋሀድ በሚል የቀረፃቸውን ሌሎች ፕሮግራሞች የአፈፃፀማቸውን ጉዳይ መለስ ብሎ ለመገምገም አረፍ የሚልበት ታዛና የጥሞና ጊዜ ያገኛል ብለው ተስፋ አድርገው ነበር፡፡

በመካከለኛው ምስራቅ የሚገኙ የድሩዝ ማህበረሠብ አባላት ተለይተው ከሚታወቁበት ነገሮች አንዱ ለሚኖሩበት ሀገር መንግስት ያላቸው የማያወላውል ታማኝነት ነው፡፡ በድፍን የመካከለኛው ምስራቅ ሀገራት ውስጥ በሀገሬ የሚኖሩ ድሩዞች የተቃውሞ ድምፃቸውን አሠሙብኝ ወይም ደግሞ በአመጽ ተነሱብኝ ብሎ ስሞታውን ያሠማም ሆነ የሚያሠማ መንግስት ለመድሀኒትም ቢሆን ተፈልጐ አይገኝም፡፡ በ1970ና 80ዎቹ የሊባኖስ የእርስ በርስ ጦርነት ወቅት የራሳቸውን ሚሊሻ በማቋቋም ነፍጥ አንስተው ውጊያ የገጠሙት ህልውናቸዉን አደጋ ላይ ከጣሉት ታጣቂ የሚሊሻ ቡድኖች ጋር እንጂ ከሊባኖስ መንግስት ወታደሮች ጋር አልነበረም፡፡ ቤተእስራኤሎችም በእስራኤል የሚኖሩ “ድሩዞች” አይነት ነበሩ፡፡

እግራቸዉ የእስራኤልን መሬት ገና ከመርገጡ ጀምሮ የሂብሩ ጋዜጦች መብታቸውንና ነፃነታቸውን የሚጋፋ፣ ሠብአዊ ክብራቸዉንም የሚያንቋሽሽ አስከፊ የጥላቻ ዘመቻ ሲከፍቱባቸው፤ ያይጥ ምስክር ድንቢጥ እንዲሉ ጋዜጦችንም ተከትለው የተለያዩ የእስራኤል ተቋማት፣ የተለያዩ የእስራኤል የመንግስት ባለስልጣናት፣ የሀይማኖት መሪዎችና የማህበረሠብ አባላት ተዘርዝሮ የማያልቅ የዘረኝነት በደል ሲፈጽሙባቸው በእስራኤል መንግስት ላይ የነበራቸው ተስፋና እምነት እንደተጠበቀ ነበር፡፡ ቤተእስራኤሎቹ ለእስራኤል መንግስት የነበራቸውን ክብርና እምነት እንዲህ በቀላሉ እሰየው ብለው ለድርድር የሚያቀርቡት ጉዳይ ጨርሶ አልነበረም፡፡ የተስፋዋ ሀገራችን በሚሏት እስራኤል ይሆናል፤ ያጋጥመናልም ብለው ጨርሰው ባልገመቱት ሁኔታ ያ ሁሉ ግፍና በደል ወደው እስኪጠሉ ድረስ ሲፈራረቅባቸው የእስራኤል መንግስት በወቅቱ የሠጣቸዉ መልስ አልነበረም፡፡ በዘርና በቀለማቸው የተነሳም ኢትዮጵያ ውስጥ ይኖሩ በነበረበት ጊዜ እንኳ ማንም ብሏቸው ወይም ጠርቷቸው የማያውቀውን “ኩሽም” (ባሪያ) የሚል መዘባበቻ ሲሆኑ የእስራኤል መንግስት ግን ተፈልጐም እንኳ ሊገኝ አልቻለም ነበር፡፡ ይህ ሁሉ ሆኖ ግን ቤተእስራኤላውያን ከተጣዱበት የዘረኝነት መጥበሻ ላይ እንዳሉ በፀጥታ መገላበጥን እንጂ በሚያምኑትና በሚያከብሩት የእስራኤል መንግስት ላይ ልባቸውን ለማሻከርም ሆነ ፊታቸውን ለማጥቆር ጨርሶ አልሞከሩም፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ በዚያን ወቅት በእስራኤል መንግስት ላይ ይህን ለማድረግ የሚያስችል አንጀት አልነበራቸውም ነበር፡፡

እንደ እስራኤል ድሩዞች ተደርገው መቆጠር ጀምረው የነበሩት ቤተእስራኤሎች ማንም ሊያደርጉት ይችላሉ ብሎ ባልገመተው ሁኔታ በእስራኤል መንግስት ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ በተቃውሞ አደባባይ በመውጣት የእየሩሳሌምንና የሌሎችም የእስራኤል ታላላቅ ከተሞች ለአንድ ወር በዘለቀ ጠንካራ የተቃውም ስብሠባና ሠልፍ ቀውጢ ያደረጉት ሀይማኖታቸውን በተመለከተ በከፍተኛ ሀፍረት ላይ የጣላቸውና በእጅጉ ያሸማቀቃቸው በደል ከደረሠባቸው በኋላ ነበር፡፡ ቤተእስራኤሎች ከዚህ በፊት በከፍተኛ ትዕግስትና ሆደ ሠፊነት ይዘዋቸው የነበሩት የተለያዩ ፈርጀ ብዙ ችግሮች ሁነኛ መፍትሄ እንዲያገኙ የእስራኤል መንግስትን ሳያሠልሱ መወትወት የጀመሩትና አልፎ አልፎም የተቃውሞ ድምፃቸውን ማሠማት የጀመሩትም ከዚህ ጊዜ በኋላ ነው፡፡ የእስራኤል መንግስት ግን የቤተእስራኤሎችን ችግር የተረዳው ገልብጦ በተቃራኒው ነበር፡፡ ለእስራኤል መንግስት የቤተእስራኤሎች ችግር እውነተኛ ችግር ሳይሆን እነሱን ለማዋሀድ በሚል የሚያደረግላቸው መጠነ ሠፊ እርዳታ ስለበዛባቸው ከመቅበጣቸው የተነሳ የመጣ ችግር አድርጐ ነበር፡፡ እናም በየጊዜው የሚያቀርቡትን የመፍትሄ አቤቱታ ለማዳመጥ የሚያስችል ጊዜውም ሆነ ልቦናና የመስሚያ ጆሮ አልነበረውም፡፡

ይልቁንስ ነገሩ ሁሉ የምግብ ፍላጐት ከመብላት ጋር ይመጣና ይጨምራል እንደሚባለው ሆኖበት ነበር፡፡ እናም አንዱ ጥፋት በጊዜ የመታረም እድል ማግኘት ሳይችል በሌላኛው ላይ እየተደራረበ ሄዶ፣ ቤተእስራኤሎቹን ከተቀረው የእስራኤል ማህበረሠብ ጋር በሚገባ ለማዋሀድ በሚል በእስራኤል መንግስት ተደግሶ የነበረውን “የቅልቅሉን” ድግስ የተጠሩት እንግዶች ሊቀምሱት እንዳይችሉ አድርጐ በአሳዛኝ ሁኔታ እንጀራውን አሻገተው፣ ወጡን እጅ እጅ እንዲል አደረገው፡፡ የእስራኤል መንግስት ቤተእስራኤሎች የራሳቸውን ቤት መግዛት እንዲችሉ ለማበረታታት በሚል በሠጣቸው ብድር አማካኝነት እስከዛሬ አስር አመት ድረስ አስር ሺ አምስት መቶ የሚሆኑ ቤተእስራኤላውያን አብዛኞቹ ባለ አንድ መኝታ ቤት የሆኑ አፓርታማዎችን ወይም የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ለመግዛት ችለዋል፡፡ ከተቀሩት ውስጥ አብዛኞቹ በመንግስት የኪራይ ቤቶች ውስጥ ሲኖሩ፣ ከዛሬ አስር አመት ወዲህ ወደ እስራኤል የመጡት ደግሞ ዛሬም ድረስ በመጠለያ ጣቢያዎችና በተንቀሳቃሽ ቤቶች ውስጥ ይኖራሉ፡፡ ለቤተእስራኤሎች ተዘርግቶ የነበረው የመኖሪያ ቤት ግዢ የብድር ፕሮግራም እንደተገለፀው የተወሰኑትን የቤት ባለቤት ሊያደርጋቸው ቢችልም የሚፈለገውንና ቀድሞውኑ የታሠበለትን ውጤት ሳያመጣ እንደከሸፈ በእስራኤል ክኔሴት (ፓርላማ) ተመስክሮበታል፡፡ ለዚህ ደግሞ ከእስራኤል መንግስት ሌላ በተጠያቂነት ቀርቦ ቃሉን ሊሠጥ የሚችል ተጠያቂ አካል ሊኖር አይችልም፡፡ እንዴት ቢባል… የእስራኤል መንግስት ይህን የብድር ፕሮግራም የጀመርኩት ቤተእስራኤሎችን ለመርዳት በሚል “ቅን” መንፈስ ነው በማለት ሞቅ ያለ ፕሮፓጋንዳውን ቢለቅም ለፕሮግራሙ አፈፃፀም ሙሉ ቀልቡንና ልቡን ጨርሶ አልሠጠም ነበር፡፡ ፕሮግራሙን ለማስፈፀም የተጠቀመባቸው ስትራተጂዎች በሙሉ የተንጋደዱና አቅም ባላቸው ባለሙያዎች የተያዙና የተመሩ ጨርሶ አልነበሩም፡፡ የፕሮግራሙ ጠቅላላ አሠራርም የግብር ይውጣ ነበር፡፡

ይህን የብድር ፕሮግራም አሠራር በትኩረት በመከታተል አፈፃፀሙን በደንብ መገምገም የቻሉ የማህበራዊ ኑሮ ጥናት ባለሙያዎች፤ የእስራኤል መንግስት ቀድሞውን ቢሆን የእስራኤል “ኩሽም” የሆኑትን ቤተእስራኤሎች ከተቀረው “ናሽም” (ነጭ) የእስራኤል ማህበረሠብ ተለይተው በአንድ አካባቢ ብቻ ተከማችተው እንዲኖሩ ለማድረግ እጅግ በረቀቀ መንገድ ነድፎ ያዘጋጀው ፕሮግራም ነው እያሉ በሰላ ትችት ሲያብጠለጥሉት ኖረዋል፡፡ ይህን የባለሙያዎች ትችት ትክክል ነውም አይደለምም ብሎ መከራከሩ አጨቃጫቂ ሊሆን ይችላል፡፡ የሆኖ ሆኖ ግን የእስራኤል መንግስት በፈለገው አይነት አላማ ቢያዘጋጅም የመጨረሻው ውጤቱ ግን ከቀረበው ትችት ጋር አንድ አይነት ነበር፡፡ የመኖሪያ ቤት ለመግዛት ብድር የወሰዱ ቤተእስራኤሎች አብዛኞቹ ስራ አጥ ነበሩ፡፡ ስራ አላቸው የሚባሉትም ቢሆን እጅግ ዝቅተኛ ክፍያ በሚያስገኙ የስራ መስኮች ላይ የተሰማሩ ነበሩ፡፡ እናም ከወሰዱት ብድር ላይ ትንሽ ጨምረው በተሻሉና መካከለኛ ገቢ አላቸው ወደሚባሉትና ሁሉም አይነት የመሠረተ ልማት አገልግሎቶች በተሟሉባቸው አካባቢዎች ውስጥ ቤት ለመግዛት የሚችሉ አልነበሩም፡፡ ሁሉም በብድር ያገኙትን ገንዘብ ይዘው ያመሩት ርካሽ የመኖሪያ ቤቶች ወደሚሸጡባቸው፣ ምንም አይነት የመሠረተ ልማት አገልግሎቶች ባልተዘረጉባቸው ኋላቀርና ጭራሹኑ ወደተዘነጉት አካባቢዎች ነበር፡፡ ይህም ሁኔታ በድህነት የተቆራመዱ፣ በጨለማ የተዋጡና፣

ከሌላው የእስራኤል ህብረተሠብ በእጅጉ የተጉላሉ “የኩሽም ቤተእስራኤሎች” የመኖሪያ ጌቶዎች እንዲመሠረቱ ዋነኛ ምክንያት ለመሆን በቃ፡፡ የማታ ማታ አፍላ፣ ኪርያት ጋት፣ ኦር ይሁዳ፣ ኪርያት ማላኪህና የመሳሠሉት በተለያዩ የእስራኤል ከተሞች ውስጥ የሚገኙ ሠፈሮች “ናሽም” እስራኤላውያን ዝር የማይሉባቸዉ ወይም ዝር ሊሉባቸው በጣም የሚፈሯቸው የቤተእስራኤሎች መኖሪያ ጌቶ ሠፈሮች በመሆን አለም አቀፍ እውቅናን ለመጐናፀፍ ቻሉ፡፡ አሳ ሁልጊዜ በመረብ ብቻ አይጠመድም፡፡ የመኖሪያ ቤት ግዢ የብድር ፕሮግራሙ እንዲህ ያለ አሳዛኝ ውጤት በማስመዝገብ ሲከሸፍ፣ ብዙዎቹ ቤተእስራኤሎችና እነሱን ለመርዳት ተብለው የተቋቋሙ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የእስራኤል መንግስት ቤተእስራእሎችን ለማዋሀድ በሚል የቀረፃቸውን ሌሎች ፕሮግራሞች የአፈፃፀማቸውን ጉዳይ መለስ ብሎ ለመገምገም አረፍ የሚልበት ታዛና የጥሞና ጊዜ ያገኛል ብለው ተስፋ አድርገው ነበር፡፡ ይህንን ተስፋ ያደረጉትም “አንዴ የተሸነፈ ሁለት ጊዜ ያፍራል” የሚለው እድሜ ጠገብ የማስተዋልና የብልሀት አነጋገር መቼም ቢሆን ለእስራኤል መንግስት አይጠፋውም ከሚል ግምታቸው በመነሳት ነበር፡፡ ቶማስ ሐንዴ የተባለ ደራሲ “Mr. Nicholas” በሚል ርዕስ በ1952 ዓ.ም ባሳተመው መጽሀፍ፤ አደጋን ለመጋፈጥ የማይፈልጉ ቦቅቧቃ ሰዎች፤ ምንም ቢያደርጉ ምን በአስደናቂ ነገሮች የተሞላ ህይወት ለመኖርና አስደናቂ ውጤቶችን ለመቀዳጀት ከቶውንም አይችሉም ይላል፡፡ ይህ የቶማስ ሒንዴ አባባል በቀላልና አጭር አገላለጽ ሲቀመጥ “ጀብዱ ለጀብደኞች፣ (Adventure is for fare adventurous) ማለት ነው፡፡ ከ1973 ዓ.ም የዬም ኪፑር ጦርነት ድል ማግስት ጀምሮ እስከአሁን ድረስ በወይዘሮ ጐልዳ ሜየርም ሆነ በቤንጃሚን ናታንያሁ ጠቅላይ ሚኒስትርነት የተመራው የእስራኤል መንግስት ወታደራዊ የሆነውን ነገር ለጊዜው ትተን ማህበራዊ ጉዳዮችን ብቻ በተመለከተ የወሠዳቸውን የተለያዩ የፖሊሲም ሆነ ሌሎች እርምጃዎችን በስሱ በመገምገም ብቻ የእስራኤል መንግስት ጀብዱ (Adventure) አድናቂና ጀብደኛ (Adventurous) መንግስት እንደሆነ ለመገንዘብ ምንም አይነት የአዕምሮ ብሩህነትን አይጠይቅም፡፡

አሳዛኙ ነገር ግን እነዚያ ቤተእስራኤሎችና የቤተእስራኤል ድርጅቶች ይህንን በወጉ መገንዘብ አለመቻላቸው አሊያም ጨርሰው መዘንጋታቸው ነበር፡፡ በዚህ የተነሳም የእስራኤል መንግስት፤ የመጀመሪያው ውሸት ወደ ሁለተኛው ውሸት ይመራል እንደሚባለው አይነት ከመጀመሪያው ስህተት ወደ ሁለተኛው ተሸጋገረ፡፡ የእስራኤል መንግስት ቤተእስራኤሎችን ለማዋሃድ በነደፈው ማስተር ፕላን፣ የስራ እድልን በተመለከተ ያስቀመጠው ዋነኛው ግቡ ለቤተእስራኤሎች የሙያና የክህሎት ስልጠና መስጠት የሚል ነው፡፡ በዚህ መሠረት የእስራኤል የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ለቤተእስራኤሎቹ በቂያቸው ነው ብሎ የመረጠላቸው የሙያና የክህሎት የስልጠና መስኮች የብረታብረት፣ የእንጨት ስራ፣ የነርሲንግ፣ የሆቴል መስተንግዶና፣ የልብስ ስፌት ናቸው፡፡ የእውነት ለመናገር ባለእጅነትን አምላክ ሁልጊዜ ለቤተእስራኤሎች ብሎ የጣፈው ሙያ ይመስላል፡፡ ይህ ላይ ላዩን ሲያዩት አሪፍ ነገር ይመስላል፡፡ ነገር ግን ቤተእስራኤሎች አስቀድሞ በተመረጠላቸውና በተወሰነባቸው በእነዚህ የስልጠና መስኮች የሙያ ስልጠና እንዲወስዱ ዝግጅት እየተደረገ ባለበት ወቅትም ሆነ ከዚያ ቀደም ብሎ እነዚህ የስራ መስኮች በፍልስጤማውያንና በሌሎች ዜጐች ከአፍ እስከደገፋቸው ተይዘው ነበር፡፡ እናም ቤተእስራኤሎቹ እንደታሰበው ሰልጥነው ቢወጡም፣ በእስራኤል የስራ እድል መድረክ ላይ ተወዳድረው ስራ ማግኘት በእጅጉ አዳጋች ሆነባቸው፡፡ በመጨረሻም ያተረፉት ነገር የእስራኤልን አውራጐዳናዎች ማጽዳት፣ መናኛ ስራዎችን እጅግ መናኛ በሆነ ክፍያ መስራትና የእስራኤል የአዲስ መጤዎችና የውህደት ሚኒስቴር የሁልጊዜም የእርዳታ ጥገኛ ሆኖ መቅረትን ነበር፡፡ በትምህርትና በሌሎች የማህበራዊ ዘርፎች የተገኘው ውጤትም ከዚህ ጨርሶ የተለየ አልነበረም፡፡ ቤተእስራኤላውያን በተሻለ ተዋህደውበታል ተብሎ ሊጠቀስ የሚችለው ተቋም ቢኖር የእስራኤል የጦር ሀይል ብቻ ነው፡፡

ቤተእስራኤሎች እውነተኛ እስራኤላዊ መሆናቸውንና ለእስራኤል ያላቸውን ፍቅርና ታማኝነት የህይወት መስዋዕትነትም ቢሆን በመክፈል ለማሳየት ቁርጠኛ አላማ የያዘና ለዚህም የምራቸውን የተዘጋጁ ነበሩ፡፡ የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊትን በገፍ የተቀላቀሉትም በዚህ የተነሳ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ በዚህ ተቋምም ቢሆን ያጋጠማቸው የዘረኝነት መድልዎ እንዲህ በቀላሉ ተነግሮ የሚያልቅ አይደለም፡፡ የእስራኤል መንግስት ችግሮቹን በጊዜ ለመፍታት ባለመቻሉ ሳይሆን ፈጽሞ ባለመፈለጉ የተነሳ በሁሉም ነገር የመጨረሻውን ዝቃጭ ደረጃ የያዘ አንድ የእስራኤል ማህበረሠብ ለመፍጠር ቻለ፡፡ ቤተእስራኤሎችም የማታ ማታ ከመላው የእስራኤል ማህበረሠብ ተለይተው የዘረኝነት ጥቃትና መድልዎ ሰለባ ሆነውና የመጨረሻውን ዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ይዘው ራሳቸውን አገኙት፡፡ ይህም ሁኔታ የአብዛኞቹን ቤተእስራኤሎች ቤተሠብ ክፉኛ አመሠቃቀለው፡፡ በእድሜ የገፉት ለከፍተኛ ግራ መጋባት ሲዳረጉ፣ ወጣቶቹ ደግሞ በከፍተኛ የማንነት ቀውስ ውስጥ በመውደቃቸው “ራስታ” ለመሆን ባዘኑ፡፡ እነዚሁ ቤተእስራኤሎች በከፍተኛ የተስፋ መቁረጥ ስሜት ውስጥ ስለወደቁ፣ በወንጀል ድርጊት መሳተፍ፣ የወንጀል ቡድን አባል መሆን፣ አደንዛዥ እጽ መጠቀምና ማዘዋወር ድርጊት ውስጥ መሳተፍ ጀመሩ፡፡

በዚህም የተነሳ የቤተእስራኤል ወጣቶች የእስራኤልን እስር ቤቶች ማጨናነቅ ተያያዙት፡፡ ለህይወት ጉጉት ማጣታቸውና ከህይወት ትግል ማፈግፈጋቸውም መገዳደልንና ራስን ማጥፋትን እንደ ዋነኛ የችግር መገላገያ መፍትሄ አድርገው ይቆጥሩት ጀመር፡፡ የተቀረው የእስራኤል ህዝብ በአባታቸው ኖህ እንደተባረኩት ልጆች እንደ ሴምና ያፌት ናቸው፡፡ ማርና ወተቱን እለት ተዕለት እየተቆጣጠረ የቆዳ ስልቻቸውን የሚሞላላቸው የራሳቸው አሳላፊ አላቸው፡፡ የቤተእስራኤሎች ኩባያ ግን ባዶ ነው፡፡ ምክንያቱም ከሀገሪቱ የማርና የወተት ሠልፍ የእነሱ ተራ ከሁሉም የመጨረሻው ስለሆነ ነው፡፡ አሁን እነሱ ለአምላካቸው እያቀረቡት ያለው ፀሎት አንድ ብቻ ነው፡፡ አምላካቸው የራሳቸውን ነህምያ (ነቢይ) እንዲሠጣቸው!! አሜን ያድርግላቸው!

መልክአ፣ ኢትዮጵያ ፪

አሁንም ከአትላንታ ጆርጅያ አልወጣኹም፡፡ ባለፈው ሣምንት ጽሑፌን ለዛሬ ያቆየኹት በራቁት ዳንስ ቤት (Strip Club) ውስጥ በአግራሞት ስለተመለከትኋት ሐበሻዊ - መልክ - ራቁት - ደናሽ ልተርክላችኹ ቀጠሮ ይዤ ነበርና ከዚያው ልቀጥልላችኹ፡፡ ዓርብ እና ቅዳሜ የአሜሪካኖቹ የመዝናኛ ዕለታት ናቸው፡፡ ማታ ወጥቶ መዝናናት የሚያሰኘው ካለ ዓርብ እስኪመጣ መጠበቅ ግዴታው ነው፡፡ ከዚያ ውጭ ባሉት ቀናት ወደ ምሽት መዝናኛ ቤቶች ጐራ ማለት የብርዳም (ቁራጭ) ምሽቶች ሰለባ ያደርጋል። መዝናኛ ቤቶቹ ዐይነታቸው ለየቅል ነው። የአትላንታ ምሽት ቤቶችም እንደ ሌሎቹ የአሜሪካ ከተሞች ሁሉ ዓርብን መስለዋል። መኪና ማቆሚያዎች በተሽከርካሪዎች፣ መግቢያ በሮች ደግሞ በሰው ተጨናንቀዋል። በከተማው ይገኛሉ ሲባል ከሰማኋቸው ራቁት ዳንስ ቤቶች ሁሉ እኔ አሁን ያለሁበትን መርጫለኹ፡፡ ሐበሻዊ መልክ ያላት ደናሽ በዚህ ቤት ትገኛለችና፡፡ ቀናት በፈጀ ልመና ቦታውን ሊያስጐበኙኝ ፈቃደኛ ሆነው ያካሄዱኝ ሦስት ወንድ ጓደኞቼ ዓርብ እና ቅዳሜ ተመራጭ ቀናት መሆናቸውን በመጠቆም ይዘውኝ የወጡት በአንዱ ዓርብ ነው፡፡ ከቦታው ደረስን፡፡

ከፊት ለፊታችን በተንጣለለው የመኪና ማቆሚያ ላይ ስፍር ቁጥር የሌላቸው መኪኖች ተደርድረዋል። ዙሪያ ገባውን በተደረገ ፍለጋ እንደምንም አንድ ማቆሚያ ተገኘ፡፡ መኪናችንን ግራና ቀኙን ጠብቆ ያለምንም ስሕተት ለማቆም የሁሉም ሰው ርዳታ አስፈልጐ ነበር፡፡ ቀድመው ቦታ ይዘው በቆሙት መኪኖች ላይ ጭረት ማሳረፍ በቀላሉ የሚታለፍ ጥፋት አይደለም፡፡ በፊልም እና በማስታወቂያ የማውቃቸው የዓለም ውድ ሞዴል መኪኖች በመኪና ማቆሚያው ከተደረደሩት መካከል ቀላል የማይባለውን ቁጥር ይዘዋል፡፡ የቤቱ መለዮ የኾነው ማስታወቂያ ከሩቅ ይጣራል፡፡ በዐሥራ አምስት ደረጃዎች ከፍታ በተሠራ የቪላ ቤት ቅርጽ ግዙፍ ቤት አናት ላይ “Pink Pony” የሚል ማስታወቂያ ተለጥፎበታል፡፡ በታላላቅ ፊደላት የተቀረጸ ሲሆን ሮዝ መልክ ባለው መብራት ያሸበረቀ ነው፡፡ በሁለቱ ቃላት መካከል ፊቷን ያዞረች ራቁት ደናሽ ሴት ምስል ተጣምሮ ተሰቅሏል። ወደ መግቢያው ስንጠጋ ሁለት ሙሉ ጥቁር የፖሊስ ልብስ የለበሱ ነጭ ጠባቂዎች ዙሪያቸውን መሣሪያ ታጥቀው ወደ ዳንስ ቤቱ የሚገቡት ሰዎች ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች አለመሆኑን መታወቂያ እያገላበጡ በማየት የይለፍ ምልክት ይሰጣሉ። ተራችንን ጠብቀን የይለፍ ማኅተሙን እጃችን ላይ ካስመታን በኋላ ተራ በተራ ፍተሻችንን እያጠናቀቅን የመግቢያ ክፍያ ወደሚከፈልበት ቦታ ሄድን፡፡

ለአንድ ሰው መግቢያ 15 ዶላር ይከፈል ነበርና ለአራታችን ለመክፈል ወደ ሒሳብ ተቀባዩዋ ስንጠጋ፣ ወደኋላ ቀርቶ የነበረው ታክሲ አሽከርካሪ ጓደኛችን ለሒሳብ ተቀባዩዋ የሆነ ምልክት አሳያት፤ የገባት አልመሰለኝም፤ ምን እንደሚል ደግማ ጠየቀችው፡፡ ባለታክሲ መሆኑንና ደንበኞችን ይዞ መምጣቱን ጠቆማት፡፡ “ገባኝ” በሚል ስሜት እየተፍለቀለቀች የኛን ወስዳ የሱን መለሰችልን፡፡ ኢትዮጵያውያን ባለታክሲዎች ደንበኛ ይዘው ወደዚህ ቤት ከመጡ መግቢያ ሳይከፍሉ ገብተው ይታደማሉ ወይም ደግሞ ኮሚሽን ይቀበላሉ፡፡ በአሜሪካ ከአምስት ኢትዮጵያውያን ጋር የመገናኘት ዕድል ቢገጥማችሁ አንዱ ባለታክሲ መሆኑ ግድ ነውና እዚህ ቤትም አብረውኝ ከመጡት ጓደኞቼ አንዱ ባለታክሲ ነው፡፡ እንዲህ ላለው የከተማ ወሬ ከእነሱ የቀረበ ስለማይኖር ጥያቄዬን ለሱው መወርወር ጀመርኹ፡፡ “የዳንስ ቤቱ ጠባቂዎች ይህን ሁሉ ሽጉጥ የታጠቁት ለምንድነው?” ስል ጠየቅኹት፡፡ “የትኞቹ? በር ላይ ያለፍናቸው ነው? ፖሊሶች ናቸዋ” አለኝ፡፡ እንደገና ወደኋላ ተመልሼ መታወቂያቸውን መጠየቅ አማረኝ። በራቁት ዳንስ ቤት መግቢያ በር ላይ ፖሊሶች ቆመው በትጋት ይቆጣጠራሉ። “ለዐቅመ አዳምና ሔዋን የደረሳችሁ እንደፍጥራጥራችሁ” በሚል ስሜት ወደ ውስጥ ያሳልፋሉ፡፡ የቆረጥነውን ትኬት ሁለተኛው በር ላይ ላገኘነው ተቆጣጣሪ ሰጥተን ወደ ውስጥ ዘለቅን፡፡ በሩ ወለል ብሎ ሲከፈት ድፍረቴ ጥሎኝ ጠፋ፡፡ ሰውነቴ በላብ ተዘፈቀ፡፡ ከወደፊት ይልቅ ወደኋላ የመመለስ ፍላጐቴ ጨመረ፡፡ የደም ግፊት እንዳለበት ሰው የጭንቅላቴን የኋለኛ ክፍል ጨምድዶ ያዘኝ። በድንጋጤ ክው ብዬ ቀረኹ፡፡ ወድጄ እና ፈቅጄ የመጣሁ ሳይሆን የሆነ ሰው በሲዖል ደጃፍ አምጥቶ የጣለኝ መሰለኝ፡፡

ዐይኔ ለጊዜው ማስተዋል የቻለው አንድ ነገር ብቻ ነው፤ እጅግ ሰፊ በሆነው ዳንስ ቤት ውስጥ ርቃናቸውን የሆኑ በርካታ ሴቶች ይርመሰመሳሉ፡፡ ከዚህ ቀደም አዲስ አበባ ውስጥ በጐበኘኋቸው “ስም ያወጡ” ራቁት ዳንስ ቤቶች ውስጥ የተመለከትኋቸው ኢትዮጵያውያን እንስቶች “በስንት ጣዕማቸው?” አሰኘኝ፡፡ ጡታቸውን እና ሃፍረተ -ገላቸውን በእራፊ ጨርቅም ቢሆን ሸፈን ያደርጉታል፡፡ ያኔ ይህን ቢዝነስ ሠለጠኑ ከተባሉት አገሮች ቀድተው አዲስ አበባ ያመጡትን የዳንስ ቤት ባለቤቶች ረግሜያቸው ነበር፡፡ ዛሬ ግን ለእራፊ ጨርቃቸውም ቢሆን አመሰገንኋቸው፡፡ ያጋነንኹ ካልመሰላችሁ እውነቱን ልንገራችኹ፡፡ ከቆምኹበት ብንቀሳቀስ የምወድቅ ስለመሰለኝ አንገቴን ወደ መሬት ቀብሬ ትንሽ ትንፋሽ ወሰድኹ፡፡ ጐትቼ ያመጣኋቸው ወዳጆቼ ወኔ ሲከዳኝ ሲያዩኝ ተሣሣቁብኝ፡፡ ከፊል እርቃኗን የኾነች አስተናጋጅ ፊቷን እንደ ጸዳል አብርታ በሚያብረቀርቅ ፈገግታ “ቁጥራችሁን ንገሩኝና ቦታ ልስጣችሁ?” ስትል ጠየቀች። ባይሆን ከለል ያለ ቦታ እንዳለ ለማየት እንደምንም ተጣጥሬ ቀና አልኹ፡፡ የቤቱ ስፋት በአንድ ጊዜ ይህን ለመቃኘት አያስችልም፡፡ ቀና ማለቴ ከፈራኋቸው ራቁት ሰውነቶች ጋር መልሶ አገጣጠመኝ፡፡ “የቱ ጋር እንቀመጥ?” በሚል ጠያቂ አስተያየት ሁሉም ወደ እኔ ተመለከቱ “ያስመጣሽን አንቺ ነሽ፤ እንግዲህ ተወጪው ይመስልባቸዋል፡፡ ከለል ያለ ቦታ ካገኘን ብዬ ከእነድንጋጤዬ ጠየቅኋቸው፡፡

ባለታክሲው ወዳጄ “ለዚች ልብሽ ነው እንዴ?” ሲል በድንጋጤዬ ላይ አላገጠብኝ፡፡ በቤተኝነት ስሜትም ከቤቱ መግቢያ በር በስተቀኝ በኩል ካለው የመጠጥ መሸጫ ክብ ባንኮኒ ላይ እንድንቀመጥ ወደዚያው ወሰደን፡፡ በዙሪያ ገባው ምን እየተከናወነ እንደሆነ የማየት አቅም ለጊዜው ስላጣሁ ዐይኔን በክቡ ባንኮኒ ውስጥ ቆመው መጠጥ በሚሸጡት ሴት እና ወንዶች ላይ ተከልኹ፡፡ አማራጭ ማጣት ኾኖብኝ እንጂ እኒህም የሚታዩ ሆነው አልነበረም፡፡ አንዳንዶቹ በውስጥ ሱሪ እና በጡት ማስያዣያ፣ ከፊሎቹ አጭር ቁምጣ በተጣበቀ አላባሽ፣ ከሰውነታቸው ከፊሉን አራቁተው ለማሻሻጫነት የቆሙ ናቸው፡፡ የአዲስ አበቦቹን “ከፊል ራቁት ደናሾች” ከእራፊው ጨርቅ በመለስ ያለውን ገላቸውን አጋልጠው ለሽያጭ በማቅረብ በቀጫጭን ብረቶች ታግዘው፣ ሰውነታቸውን ከወሲብ ቀስቃሽ ሙዚቃ ጋር አዋሕደው እየተገለባበጡ የሽልማት ገንዘብ ሲሰበስቡ ሳይ “አይ ድህነት አያደርገው የለ” ስል ለእንስቶቹ ሆዴ ተላውሶላቸው ነበር፡፡ በርካቶች ሥራ ፍለጋ በሚሰደዱባት የዓለም ቁንጮ በሆነችው ሀገረ አሜሪካ፣ ገላቸውን ለሽያጭ ላቀረቡት ወጣት እንስቶችስ “አይ የእንጀራ ነገር” ስል ደረቴን ልድቃላቸው ይሆን? ጉዳዩ የእንጀራ አይመስልም፤ እናም ደረት የመድቃቱ ነገር አስፈላጊ አልመሰለኝም፡፡ ቀስ እያልኹ የቤቱን መብራት እና ድምፅ ተላመድኹት፡፡ አቀማመጤን አስተካክዬም ሰረቅ እያደረግሁ ቀረብ ካሉት “የገላ ነጋዴዎች” ቅኝቴን ጀመርኹ። የቤቱ አጠቃላይ ስፋት በግምት ሁለት ሺሕ ካሬ ሜትር ላይ ያረፈ እጅግ ሰፊ ወጥ አዳራሽ ነው፤ ግን ደግሞ በተለያየ መንገድ ተከፋፍሏል፡፡ አራት መዓዝን ቅርጽ ያላቸው ሰፋፊ የመጠጥ መሸጫ ባንኮኒዎች፣ በርካታ የመደነሻ መድረኮች አሉት፡፡

ነጭ እና ጥቁር ቀለም ያላቸው ሴቶች ተራ በተራ ወደ መድረኩ እየመጡ የዕርቃን ትርኢት ያሳያሉ፤ ጨርሰው ሲወርዱም ግብዣ ያቀረበላቸውን ሰው ይዘው በአንደኛው የቤቱ ኮርነር በርከት ብለው ወደተደረደሩትና የመኝታ ያህል ተለጥጠው የሶፋ መቀመጫዎች ይዘው እየሄዱ ሥራቸውን በግል ይቀጥላሉ። ልዩ ክፍያ የሚከፍል ደግሞ ሴቶቹን ወደውስጠኛው ክፍል ይዞ እንዲገባ ይፈቀድለታል፡፡ “እዚህ ቤት ግን በርግጥ ኢትዮጵያውያን ይመጣሉ?” - ቀደም ሲል የሰማሁትን መረጃ ተጠራጥሬ እንደገና ለማረጋገጥ ለባለታክሲው ያቀረብኹለት ጥያቄ ነው፡፡ በርግጥ ጥያቄው የሞኝ ይመስላል፡፡ በአዲስ አበባዎቹ የምሽት ዳንስ ቤቶች ውስጥ ተገኝተው በአዳጊ እንስቶች የውስጥ ሱሪ ገንዘብ እየጨመሩ የሚዝናኑ ኢትዮጵያውያንን በኢትዮጵያ ምድር አይቼ እንዲህ በዘመነች አገር የኢትዮጵያ ልጆች ታዳሚ መሆናቸውን መጠየቅ በርግጥ “ሞኝነት” ነው፡፡ ግን ደግሞ የቤቱን አስነዋሪነት ስመለከት በዚህ ቦታ የሀገሬ ልጆች ተሳታፊም ታዳሚም ናቸው መባሉን አምኖ መቀበል ከባድ ኾነብኝ፡፡ መብሰክሰኬ ብዙም ሳይቆይ ከጓደኞቼ የአሻግረሽ ተመልከቺ የቀስታ ጥቆማ ደረሰኝ። በቀላሉ አልታይ አለኝ፡፡ ከተቀመጥኹበት ረጅሙ የባንኮኒ ወንበር ተንጠራርቼ ዐይኔን አሻገርኹ፡፡ ከፍ ካሉት የመደነሻ መድረኮች ዝቅ ብለው ከተደረደሩት መቀመጫዎች ላይ አንዲት ሴት እና ሁለት ወንዶች ተቀምጠው እንቅስቃሴውን ፈዘው ያስተውላሉ፡፡ በመጠጥ ጭምር እየተዝናኑም ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ያየኋቸው ከርቀት ቢሆንም ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን መለየት አላስቸገረኝም፡፡ ባያውቁኝ ባላውቃቸውም እዚያ ቦታ ቁጭ ብዬ በሌላ የሀገሬ ሰው በመታየቴ ብቻ ሃፍረት ተሰምቶኝ ለመደበቅ ሞከርኹ፡፡ እነርሱ እኔ የተሰማኝ ስሜት የተሰማቸው አልመሰለኝም፡፡ ማንም በዚያ ቦታ ቢኖር ግድ ያላቸው አይመስሉም፡፡ እንደ ውጭ አገር ዜጐቹ ሁሉ እነርሱም ተራ በተራ እየተነሡ ዶላር ይሸልማሉ፡፡

በቃል ያልተመለሰው ጥያቄዬ በተግባር ተመለሰልኝ፡፡ ኢትዮጵያውያኑ በዚያ ቤት ነበሩ፡፡ ባለታክሲው ወዳጄም፤ “የኛ አገር ልጆች በብዛት የዚህ ቤት ደንበኛ አይደሉም። አልፎ አልፎ የእኔ ቢጤ ባለታክሲ ደንበኛ ይዞ ይመጣል፡፡ አንዳንዴ ደግሞ እንዲህ እንዳንቺ እንግዳ እና አዲስ ሰው ከሀገር ቤት ሲመጣ አሳዩኝ ይልና ለማየት ይመጣል፡፡ ግን ከአንድ ቀን በላይ እዚህ ቤት የሚመጣ ኢትዮጵያዊ በጣም ጥቂት ነው፡፡ አንዳንዱ እዚህ በመምጣቱ ብቻ ራሱን እንደረከሰ ሰው ቆጥሮ ቤተ ክርስቲያን ሄዶ ጠበል ይጠመቃል አትላንታ ካለው ኢትዮጵያዊ በጣም ጥቂት ቁጥር የሚይዙ ሰዎች ግን የቤቱ ደንበኞች ናቸው፡፡እንዲህ ያለ ቤት ስለመኖሩ የማያውቁ ደግሞ በርካቶች ናቸው፤” አለኝ። የቤቱን ታዳሚዎች ኹኔታ በግምታዊ አኅዝ ለማስቀመጥ 300 በሚሆኑ እንግዶች መካከል ከ70 በላይ የሚሆኑ እርቃን ሴቶች ይርመሰመሳሉ፡፡ ከእኔ ጥያቄ እና ከባለታክሲው ወዳጄ መልስ ውጪ በመካከላችን ጸጥታ ሰፍኗል፡፡ ሁለቱ አገጫቸውን እጃቸው ላይ አስደግፈው ጸጥ ብለዋል፤ ተፋፍረዋልም፡፡ እውነት ነው፤ እንዲህ ያለውን ነገር አንድ ላይ ኾኖ መመልከት በራሱ ያስተፋፍራል፡፡ በቤቱ እንደምትሠራ የተነገረኝ አበሻዊ መልክ ያላት ደናሽ አለመምጣት ካሰለቸኝ ከአንድ ሰዓት በኋላ “መጣችልሽ፣ መጣችልሽ!” አለኝ ባለታክሲው ወዳጄ፡፡ ክንፍ ያለኝ ይመስል አኮበኮብኹ፤ ልጅቱን ፍለጋ አንገቴን አንቀዠቀዠኹት፡፡ መካከል ላይ ወዳለው መድረክ የምታመራ፣ ያማረ ተክለሰውነት ወዳላት ወጣት አሳየኝ፡፡ ወደ መድረኩ እየሄደች ስለሆነ ፊቷን ማየት አልቻልኹም፡፡ የሚታየኝ ጀርባዋ ነበር፡፡ አዲስ አበባ እንዳየኋቸው ሴቶች ከእራፊ በላይ በሆነ ጨርቅ ሰውነቷን ሸፍናለች፡፡ ጡቶቿን ሙሉ ለሙሉ የሚሸፍን ጡት ማስያዣ እና ሣሣ ያለም ቢሆን ታፋዋ ድረስ የሚሸፍን ቁምጣ መሰል ነገር ለብሳለች፡፡ ትልቅ ተረከዝ ያለው ቡትስ ጫማም ተጫምታለች፡፡ መድረኩን አስቀድማ ስትደንስበት ከነበረችው ባለነጭ ገላ ሴት ተረክባ የተከፈተላትን የሙዚቃ ምት ተከትላ፣ ቀስ እያለች ወደ መድረኩ ወጣች። ዙሪያውን ከበው የተቀመጡት ታዳሚዎች የቀደመችውን በጭብጨባ ሸኝተው እሷንም በጭብጨባ ተቀበሉ፡፡ የእኔ ዐይን እንዳፈጠጠ ነው፡፡ ጭንቅላቷ በአርተፊሻል፣ ፀጉር ቢሸፈንም መልኳ ሐበሻዊ መሆኑን ለመለየት ነጋሪ አላስፈለገኝም፡፡ በዝግታ የጀመረችውን ዳንስ እያፈጠነችው መጣች፡፡ ሰውነቷ በከፊል የተሸፈነ መሆኑን ስመለከት፣ ምናልባት አንዳች ማኅበረሰባዊ ሞራል በጥቂቱም ቢሆን ተጭኗት ሊሆን ይችላል ስል ጠረጠርኩኹ፤ ግን ደግሞ በቤቱ ውስጥ ከደናሾቹ እንደ አንዷ ኾና መድረክ ላይ ከወጣች በኋላ፣ ሰውነትን በእራፊ ጨርቅ መሸፈኑ ትርጉም አልባ ሆነብኝ፡፡ መጀመሪያውኑ ተወልቆ የተጣለ ነገር ነውና። ልጅቱ እንቅስቃሴዋን ቀጥላለች፡፡

ከመድረኩ ጀምረው ወደላይ የቤቱን አናት እንደምሰሶ ደግፈው የያዙትንና ለዚሁ አገልግሎት ተብለው የተዘጋጁትን ቀጫጭን ብረቶች እየተጠቀመች ስሜትን ለወሲብ በሚቀሰቅስ እንቅስቃሴ ለደቂቃዎች ስትናጥ ቆየች፡፡ ቀጠለችና አንዱን ብረት በአንድ እጇ እንደያዘች የአንድ እግር ጫማዋን አወለቀች፤ አስከትላም ሁለተኛውን ደገመች። በመድረኩ የጽዳት እና የዶላር ሽልማት ሰብሳቢ ሠራተኛ አማካኝነት የወለቀው ጫማ ተነሣ፡፡ ዳንሱ በባዶ እግር ቀጠለ፡፡ ቆየት ብላ የጡት ማስያዣዋን ፈታ ጥላ ከወገቧ በላይ እርቃኗን ሆነች፡፡ “ኦ! አምላኬ! የፈጣሪን ስም ጠራሁ። ሸላሚዎች ተነሡ፡፡ መጠኑ ስንት እንደሆነ መለየት ባልችልም ዶላር ይዘንብላት ገባ፡፡ ቆየት ብዬ እንደተረዳሁት ከቤቱ ደንበኞች ውስጥ ከዐሥር እስከ 100 ዶላር የሚሰጡ ባይጠፉም አብዛኛው ደንበኛ ግን ዘርዝሮ ይዞ አጠገባቸው ይቆምና በተለያየ ስልት እየስደነሰ ዶላሩ አምስት እና ዐሥር ላይ ሲደርስ ቦታው ሄዶ ይቀመጣል፡፡ በቤቱ ውስጥ ራቁት ደናሾቹ በመድረኩ ላይ እያሉ እያዩ ከማስደነስ ውጪ ቀርቦ መንካት የተከለከለ ነው፡፡ ልጅቷ ዳንሷንም እራፊ ጨርቋንም ከሰውነቷ ላይ እያነሣች መጣል ቀጥላለች፡፡ ሥሡን ቁምጣዋን አውልቃ ጥላ በውስጥ ሱሪ ብቻ ቀርታለች፡፡እየተዟዟረች ሽልማቷን ትሰበስባለች፡፡ አዲስ አበባ ላይ ደናሾቹን ባገኘሁ ጊዜ ዳንሱን ሥራ ብለው የያዙት አማራጭ ከማጣት ተነሥተው እንደሆነ አንጀት በሚበላ የችግር ታሪካቸው አዋዝተው ተርከውልኝ ነበር፡፡

በተለይ አንዲት 18 ዓመት በቅጡ የማይሞላት አዳጊ፤ “በትምህርቴ ብዙም ሳልገፋ እናት እና አባቴ ሁለት ታናናሾች ጥለውብኝ ሞተው እነሱን አስተምራለሁ፡፡ የምንኖረው በቀበሌ ቤት ውስጥ ነው፡፡ ረኀብ እና ጥማት ተራ በተራ እየተፈራረቀ ችግር የቤታችን አባል ቢሆንብኝ አንዷን ጐረቤት ተከትዬ ገላዬን ለመሸጥ ጐዳና ወጣሁ፤ ጓደኛዬ እዚህ የመቀጠር ዕድል ሲቀናት ለእኔ ደግሞ መንገዱን አሳየችኝ፤ ከመራብ ገላን መሸጥ፣ ገላን ከመሸጥ ደግሞ አሳይቶ ገንዘብ ማግኘት አይሻልም?” ስትልም ጠይቃኝ ነበር፡፡ ያን ጊዜ “መራብ ይሻላል” እንዳልላት እሷ ሥራውን የመረጠችው መራብ ባስከተለባት መዘዝ እንደሆነ ነግራኛለች። መራብ የሚያመጣውን መዘዝ ደግሞ ምን እንደሚያስታውሰን አላውቀውምና ዝም አልኋት፡፡ የጀመርሽው መንገድ የተሻለ ነው እንዳልል ደግሞ ድርጊቱ አስነውሮኛል። እናም ያኔ ከንፈሬን በሐዘኔታ መጥጬ በደንብ ዝም አልኳት፡፡ ይቺኛዋን ግን ምን ልበላት፡፡ እኔ እሷን እያየሁ ሐሳቤን ሳነሣ ስጥል፣ እርሷ ልብሷን ጥላ ጨርሳ በመጨረሻም እርቃን ገላዋን፣ መለመላዋን ቀርታለች፡፡ አሁን እኔም ኢትዮጵያዊ እንዳትሆን አጥብቄ ተመኘሁ። ይኼኔ እኮ እንዲህ ሆና የምታገኘውን ዶላር ከምትልክላቸው ቤተሰቦቿ ውስጥ አንዱ ወንድሟ እየፈነጨበት ይሆናል ስል አሰብኹ፡፡ የተቀመጡትም የቆሙትም ወንዶቹ በራቁት ገላዋ አፋቸውን ከፍተዋል፡፡ በዛ ሰዓት የሚደንሰው ራቁት ሰውነት የእርሷ ብቻ አልነበረም፡፡ በርካቶች ሥራ ያሉትን እርቃን ዳንስ ተያይዘውታል፡፡

ምን ያህል ሰዓት መድረክ ላይ እንደቆየች ለማስተዋል ባልችልም ሲበቃት ወረደች፡፡ መጨረሻዋን ለማየት በዓይኔ ተከተልኳት፡፡ እንደ ባልደረቦቿ እሷም የመድረኩን ካበቃች በኋላ የግሏን ጀመረች። ተጠርታ መሰለኝ ከወንዶች ጋር ተቀምጣ ስታያት ወደ ነበረች ወጣት ፈረንጅ ሴት ሄዳ ትደንስላት ጀመረች። የዳንሱ እንቅስቃሴ መተሻሸትንም ይጨምር ነበር፡፡ ሲላት ደግሞ ትቀመጥበታለች። ልጅቷን ከዛ በላይ ተከታትሎ መመልከት ለእኔ ሕመም ሆነብኝ፡፡ እንደምንም ብዬ ላነጋግራት ሞከርኩ፡፡ በጉዳዩ ላይ ከወዳጆቼ ጋር ተወያየሁ፡፡ ለማነጋገር ያለው አንድ አማራጭ ለዳንስ መጋበዝ ብቻ ሆኖ ተገኘ። ማነው የሚጋብዘው? ደፋር ከመካከላችን ጠፋ፡፡ እንደምንም ለትንሽ ደቂቃ ብዬ ባለታክሲውን አግባባሁት፡፡ በአንዷ አስተናጋጅ አማካይነት ጥሪ ተላለፈላት፡፡ ቆየት ብላ በውስጥ ሱሪ እና በጡት ማስያዣ መጣች፡፡ ቁርጥ ሐበሻ። እንደመጣች ባለታክሲውን እየተሻሸች መደነስ ጀመረች፡፡ ከየት እንደመጣች ለማወቅ በአማርኛ ሰላምታ ሰጠኋት። በማውቃቸው ጥቂት ትግርኛ ቋንቋ ሞከርኋት፡፡ አሁንም ዝም አለች፡፡ ባለታክሲው እየቀፈፈው መጣ፤ ሊታገሠኝ አልቻለም፡፡ ለመገፍተር የዳዳው ይመስላል። ሰላምታውን በፈረንጅ ቋንቋ አደረግሁና “የሀገሬ ልጅ መስለሽኝ ነው” አልኋት፡፡ ዳንሷን ሳታቋርጥ “የት ነው ሀገርሽ?” አለች። “ኢትዮጵያ”፣ አንገቷን በማወዛወዝ ምላሽ ሰጠችኝ፡፡ እኔ ከዛ አይደለሁም ማለቷ ነበር፡፡ “ከአሥመራ?” አሁንም አንገቷን አወዛወዘች፡፡ “መልክሽ ግን የኛን አገር ሰው ይመስላል” አልኋት፤ ዝም ብላ መወዛወዟን ቀጠለች፡፡ “ይውለቅልህ” ለባለታክሲው ጥያቄ አቀረበችለት፡፡ ያችኑ እራፊ ጨርቋን ልታወልቅ መሆኑ ነው፡፡ “አልፈልግም፤ አልፈልግም” አለና ተቻኩሎ ከኪሱ ካወጣቸው ዶላሮች መካከል አምስት ዶላር ሰጣት አሜሪካን ሀገር ባለታክሲን ከሌላው ሰው ለየት የሚያርገው በርካታ ዝርዝር ዶላሮች በኪሱ መያዙ ነው፡፡

እንደ ሌላው ሰው በየማሽኑ ላይ ካርድ ሲጭር አይውልም። “ዐሥር ዶላር ነው” ስትል አምስት ዶላር ጭማሪ ጠየቀችው፤ እንዲያቆያት በዐይኔ ብለማመነውም ፈቃደኛ አልሆነም። ዐሥር ዶላር ጨመረላትና እንድትሄድለት “አመሰግናለሁ” አላት፡፡ ምስጋናውን በፈረንጅ ቋንቋ ነበር ያቀረበላት፡፡ እሷም ዶላሩን ተቀብላው “አመሰግናለሁ” አለችው። መልሱ ግን በአማርኛ እንጂ በፈረንጅኛ አልነበረም።ሁለታችንም በድንጋጤ “እንዴ?” የሚል ቃል አወጣን፡፡ እኔማ ከተቀመጥኹበት ተነሥቼ ይዤ ላስቀራት ምንም አልቀረኝም። ፈገግ ብላ “ያቐንየለይ” ስትል ምስጋናውን በትግርኛ ጨምራልን፣ አረማመዷን አፍጥና ግራ አጋብታን ወደመጣችበት ተመለሰች፡፡ ዳንስ ቤቱን ለማየት ከመሄዴ በፊት ስለሐበሻዊ መልኳ ደናሽ የነገሩኝ ኢትዮጵያውያን ልጅቷ ኤርትራዊ ስለመሆኗ ሳይጠራጠሩ ነበር ያወሩኝ፡፡ ኤርትራውያን ባገኘሁ ጊዜም ስለዚችው ልጅ ጠይቄያቸው ኢትዮጵያዊ ስለመሆኗ ነው ያወሩኝ፡፡ አብረውኝ የመጡት ልጆችም ልጅቱ ኤርትራዊ ስለመሆኗ ቅንጣት ታክል ጥርጣሬ አልነበራቸውም፡፡ሁለቱም ከኛ ወገን አይደለችም ሲሉ፤ እዚያ እና እዚያ አሽቀንጥረው ሊጥሏት ይሞክራሉ፡፡ ዋናው ምክንያታቸው ደግሞ በድርጊቱ ማፈራቸው ነው፡፡ የልጅቷ ዜግነት የማወዛገቡ ሌላው ምክንያት ራሷ ልጅቷ መሆኗ ገባኝ። በሁለቱም ቋንቋ ትናገራለች፤ መልኳም የሐበሻ ነው፡፡ ለእኔ ግን መምጫዋ አላስጨነቀኝም፡፡ እሷ ከየትኛውም ትምጣ፤ ከሁለቱም ሀገር ቀያቸውን ጥለው የሚሰደዱ ዜጎች፤ ወይ በትምህርት፣ በፖለቲካ ጉዳይ አሊያም ሥራ ፍለጋ ነው፡፡ “እንጀራ ፍለጋ 15 ሺሕ ኪሎሜትር ተጉዞ ገላን በአደባባይ አራቁቶ ለሰፊ ሕዝብ መሸጥን ምን አመጣው?” አላናገረችኝም እንጂ ይህችንም እንደ አዲሳባዎቹ ልጠይቃት ያሰብኹት ጥያቄ ነበር፡፡

ምናልባትም “ከምራብ ብዬ” ነው ትለኝ ይሆናል፡፡ የሷ ግን እንደአዲሳባዎቹ መልስ አልባ አያደርግም፤ “ስንት እንጀራ ለመብላት ነው?” እላት ነበር፡፡ ለእኔ ሰቅጣጭ ከሆነብኝ ከዚህ ቤት ወጥተን ያመራነው ወደ ኢትዮጵያውያን ጭፈራ ቤት ነበር። መቼም “ከሺሻ እና ከዳንስ ቤት አትወጪም ወይ?” እንዳትሉኝ እኔ ያየሁት እንዳይቀርባችሁ ከሚል እሳቤ ነው!! ሌላ ሌላውንም ያየኹትን፣ የታዘብኹትን ያህል ቀስ እያልኹ አወጋችኋለሁ፡፡እናም በዚህ ጭፈራ ቤት በመጠጥ ተሟሙቀው፣ሲያሻቸው እየተሻሹ ሲላቸው እየተሳሳሙ፣ሲላቸው እየቆሙ፣ሲፈልጉ ደግሞ ተቀምጠው ሺሻቸውን እያጨሱ፤በጭሱ ደግሞ ታፍነው ልባቸው እስኪጠፋ በሀገራቸው ዘፈን እየጨፈሩ ያየኋቸው ጥንዶች እጅግ ጨዋ ሆነው ታዩኝ። የአስነዋሪ እና የአኩሪ ተግባር መለኪያው ጠፋብኝ፡፡ በአሜሪካ ቆይታዬ በአገሬ የማውቀውን የአስነዋሪ እና የአኩሪ ታሪክ መለኪያ ካጠፋብኝ ሌላው የጥቂት ኢትዮጵያውያን ተግባር አንዱ ደግሞ የግብረሰዶማውያን ነገር ነው፡፡ለአሜሪካኖቹ ሳይቀር አስጨናቂ በሆነው ግብረሰዶማዊነት ተዘፍቀው ያየኋቸውና ታሪካቸውን የሰማሁት ኢትዮጵያውያን እስካሁን አስጨንቀውኛል። ጎዳና የወጡ ኢትዮጵያውያንን ማየት እነዚህኞቹን እንደማየት አልከበደኝም፡፡ ግብረሰዶማዊነት በአሜሪካ መባባሱ እና ቀስ በቀስ በተለያዩ ግዛቶች ለጋብቻም እየተፈቀደ መሄዱ የኢትዮጵያንም ራስ ምታት ሆኗል። አንዲት እናት ለአቅመ አዳም የደረሰ ወንድ ልጇ “ማሚ ጓደኛዬን ላስተዋውቅሽ” ሲል በሰጣት ቀጠሮ ስላጋጠማት ነገር ያወጋችኝን ደግሞ እስቲ ልንገራችሁ። (ይቀጥላል)

አንዳንዴ ምን እንደማስብ ታውቃላችሁ? የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ከፖለቲካ ወገንተኝነት ፍፁም ነፃ መሆኑን የሚያረጋግጥ አዲስ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ግኝት የሚፈጥርልን ብናገኝ (ቻይናን ምን ይሳናታል?) በገንዘብ ባንችል እንኳን በ”ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ” ስም እንማጠናቸው ነበር… (ቻይና ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ስታውቅ አይደል?)

ወዳጆቼ፤ የጥምቀት በዓል እንዴት አለፈ እባካችሁ? በሸጋ ያለፈ ይመስለኛል (እኔ ከናንተ ባላውቅም) ከሁሉም ያስደመመኝ ግን ምን መሰላችሁ? በጥምቀት ይወረወር የነበረው ሎሚ ተረት ሆኖ (እንደ ድህነት? ማለት ነው) ዘንድሮ በፕሪም ተተክቷል የሚባል ነገር ሰምቻለሁ፡፡ “ወጭ ለምኔ” ያሉ የዘመኑ ወጣቶች ደግሞ (በሬ ለምኔ እንደሚባለው) የሞባይል ነምበራቸውን ቆነጃጅቱ ደረት ላይ ሲወረውሩ እንደዋሉም የአውዳመት የወሬ ምንጮቼ ሹክ ብለውኛል፡፡ በደቡብ አፍሪካው የባለፈው ሰኞ የብሄራዊ ቡድናችን ግጥምያ እለት የተባለውን ሰምታችሁልኛል? “ውበት ሲለካ የኢትዮጵያ ሴቶች ናቸው ለካ!” የሚለውን ማለቴ ነው፡፡ (ለነገሩ ሲያንሳቸው እኮ ነው!!) ነገርዬውን ዝም ብዬ ሳስበው ግን የኢትዮጵያን እንስቶች ውበት ድንገት ያጐሉት ያለፈው የአፍሪካ ዋንጫ ሻምፒዮን ከሆነችው ዛምቢያ ጋር ገጥመው (ያውም በጐደሎ ተጫዋቾች) ድንቅ የኳስ ጥበብ ያሳዩት የብሄራዊ ቡድናችን አባላት ይመስሉኛል - (ያዳኑን እነ አዳነን ማለቴ ነው!) የሴቶቻችን ውበትማ አዲስ ክስተት አይደለማ!! እኔ የምለው ግን… በኢቴቪ ቀርቦ አስተያየቱን የሰጠ አንድ

በኢትዮጵያ እግር ኳስ ያበደ አድናቂ፤ ቡድናችንን ከእነሜሲ ጋር ሁሉ ሲያነፃፅር እንደ ነበር ሰምታችኋል? (ቢጋነንም ከጋለ ስሜት የመነጨ ነው ብለን እንለፈው) በነገራችሁ ላይ… ይሄ ህዳሴያችን ብዙ ታሪኮቻችንን እያደሰልን አይመስላችሁም! (በእድል እኮ አይደለም በትጋት እንጂ!) ከህዳሴው ጋር ያልታደሰልን ዋናው የህይወታችን ክፍል ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? ያልታደለው ፖለቲካችን ብቻ!! እንኳንስ ሊታደስ ቀርቶ ጭርሱኑ ወደ ኋላ… ወደ ጥንቱ የጨለማ ዘመን (dark age) እየጐተተን፣ የዓለም መሳቂያ መሳለቂያ ሊያደርገን ዳር ዳር እያለ እኮ ነው! ፖለቲከኞችን በማሰር፣ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን ጋዜጠኞች ለስደት በመዳረግና ወህኒ ቤት በመከርቸም፣ የተቃዋሚ ፓርቲዎችን ነፃ እንቅስቃሴ በማፈን፣ በሙስናና በመልካም አስተዳደር እጦት፣ በሰብአዊ መብት ጥሰት፣ ወዘተ… ኢትዮጵያ በተደጋጋሚ ስሟ እየተነሳ መሆኑ ፀሃይ የሞቀው አደባባይ ያወቀው እውነት ነው፡፡ በእርግጥ እንዲህ ያለውን ውንጀላ ባልወለደ አንጀታቸው የሚሰነዝሩት የኢትዮጵያ በጐ ነገር የማይዋጥላቸው እንደ ሂዩማንስ ራይት ዎች ያሉ ጨለምተኛ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች እንደሆኑ ሁሌም ገዢው ፓርቲያችን ይነግረናል (እንዳንሳሳት ብሎ እኮ ነው!) ችግሩ ግን ምን መሰላችሁ? እዚሁ ከምርጫ ቦርድ ህጋዊ ሰርተፊኬት ተሰጥቷቸው የሚንቀሳቀሱትም ህጋዊ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተሟጋቹን ውንጀላ አንድም ሳያስቀሩ ይቀበሉታል፡፡

(ታዲያ ምን ተሻለ?) ምን መቀበል ብቻ… “መች ተነካና… ይታያል ገና!” ባይ ናቸው፡፡ (የገዢውን ፓርቲ ጉድ ማለታቸው እኮ ነው!) እኔ የምለው ግን… የአገር ሽማግሌዎች ቡድን መሪ የሆኑት ባለውለታችን ፕሮፌሰር ኤፍሬም ይስሃቅ ፓርቲዎችን የማስታረቅ በጐ ሚናቸውን እንዴት ዘነጉት? ለነገሩ በእሳቸውም አይፈረድም እኮ! (የአውሮፕላን ወጪ ገደላቸዋ!) እንዴ… በ97 የፖለቲካ ቀውስ ጊዜ ታስረው የነበሩትን የቅንጅት አመራሮች ከመንግስት ጋር ለማስማማት ከአሜሪካ ኢትዮጵያ የነበረውን ጉዞ የውሃ መንገድ አድርገውት ነበር እኮ! ያውም በገዛ ገንዘባቸው እየተመላለሱ፡፡ ግን ምናለ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚመላለሱበትን የአየር ትኬት ስፖንሰር ቢያደርጋቸው? (የአገር ጉዳይ አይደለም እንዴ?!) ለማንኛውም ግን ፕሮፌሰሩ አንዴ እንደምንም ወደ አገራቸው ጐራ ብለው ኢህአዴግንና ተቃዋሚዎቹን “አንተም ተው! አንተም ተው!” ቢሏቸው ሳይሻል አይቀርም ባይ ነኝ፡፡

(እረስቼው! ምርጫ ቦርድም ለካ ሌላው የፓርቲዎች የኩርፊያ ሰበብ ነው) እሱ እንኳን እርቅ ሳይሆን “ማጥራት” ነው የሚሻለው፡፡ አንዳንዴ ምን እንደማስብ ታውቃላችሁ? የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ከፖለቲካ ወገንተኝነት ፍፁም ነፃ መሆኑን የሚያረጋግጥ አዲስ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ግኝት የሚፈጥርልን ብናገኝ (ቻይናን ምን ይሳናታል?) በገንዘብ ባንችል እንኳን በ”ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ” ስም እንማጠናቸው ነበር… (ቻይና ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ስታውቅ አይደል?) እንዴ… ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ከ15 አመት በኋላ በጐ እንቅስቃሴ የጀመረው እግር ኳሳችን እንኳ የእነቬንገርን ቀልብ ስቧል እየተባለ እኮ ነው፡፡ ፖለቲካችን ግን ይኸው 21 አመት ወደኋላ መምዘግዘግ ይዞላችኋል - ያውም ህዳሴያችንን ይዞ (ወይ ነዶ አሉ!) አያችሁ… ይሄ ክፉ ፖለቲካችን የጀመርኩትን የጥምቀት ወግ ሳልጨርስ እንዴት ጐትቶ ውስጡ እንደዶለኝ! (ፖለቲካችን እርግማንና ወቀሳ ምሱ ነው አሉ!) እኔ የምለው… በዘንድሮ የጥምቀት በዓል መዲናዋ እንዴት እንደፀዳችና እንደተዋበች በደንብ አስተውላችኋል? እንዴ… ከተማዋ 125ኛ ዓመት ልደቷን አንድ አመት ሙሉ ስታከብርም እኮ እንዲህ አላማረባትም! (አክብሮ መና ይሏል ይሄ ነው!) እውነቴን ነው የምላችሁ… የመዲናዋ ወጣት በዓሉን ያከበረው “ለጥምቀት ያልሆነ ከተማ…” በሚል አዲስ ምሳሌያዊ አባባል ይመስላል፡፡

(ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ ይበጣጠስ እንዲሉ!) ቆይ ግን ያልፀዳና ያልተዋበ የመዲናዋ ስፍራ አለ እንዴ? (ማዘጋጃ ቤት ሲያሾፍ እንደኖረ የገባን አሁን ነው!) ለወትሮው የሽንትና የቆሻሻ ክምር የነበሩ ስፍራዎች ሁሉ ፀድተውና በተለያዩ ቀለማት ተኳኩለው “ሸገር” ተውሰን ያመጣናት ከተማ ልትመስለን ምን ቀራት? መርካቶ ሰባተኛ አካባቢ እንዴት በባንዲራና በፊኛ አሸበርቆ እንደነበር መስተዳድሩ አይቶት ይሆን? (ማን ነበር “ይደገም ቅዳሜ” ያለው…) ከምሬ ነው… መቼም አይቶት ከሆነ የመዲናዋ ልደት “በህዝብ ጥያቄ በድጋሚ ይከበራል” ማለቱ አይቀርም! እኔ ግን የልደቱን በድጋሚ መከበር ምንም ቢሆን እንደማልደግፍ ከወዲሁ አቋሜን ልገልፅ እወዳለሁ፡፡ እንደ 34ቱ ፓርቲዎችም ፒቲሽን ማሰባሰብ ከጀመርኩ አንድ ሁለት ቀናት አልፎኛል፡፡ አያችሁ… ባለፈው ተመክሮ እንደተገነዘብነው መስተዳድሩ የፓርቲና የፌሽታ ነገር አይሆንለትም፡፡ (ፍንዳታ ቢጤ ነው!) የመዲናዋን 125ኛ አመት ከአንድ አመት በላይ እኮ ነው ያከበረው፡፡ (ለመሆኑ ጊነስ ላይ ተመዘገበለት ይሆን?) እናላችሁ… ራሴ ያነሳሁትን የይደገም ጥያቄ ራሴ መቃወሜን እወቁልኝ፡፡ አንድ ጥያቄ ግን አለኝ፡፡ መስተዳድሩ የመዲናዋን ልደት ከአንድ አመት በላይ ሲያከብር (ራሱ ነው ያለን!) ምን ማስታወሻ የሚሆን ነገር ለከተማዋ ሰራላት? (ከፕሮፓጋንዳው ውጭ ማለቴ ነው!) ይኸውላችሁ… እኔ ከጥምቀቱ የወጣቶች ቡድን ምን ቁምነገር ቀሰምኩ መሰላችሁ? የመዲናዋ ወጣት ሲፈልግና ልቡ ያመነበት ጉዳይ ሲሆን እንደንብ መንጋ ነው - የያዘውን ስራ ዶግ አመድ ያደርገዋል፡፡ አድምቶ ይሰራዋል! (በኢህአዴግ ቋንቋ!) ይታያችሁ… የፅዳት ሠራዊት የለ! የህዝብ ንቅናቄ የለ! 1ለ5 አደረጃጀትማ ጭርሱኑ ትዝ ያለውም የለ!! አያችሁልኝ… ወጣት ባመነበት ጉዳይ ላይ እንዲህ አጀብ ያሰኛል - ያውም ያለ አንዳች የካድሬ ፕሮፓጋንዳና አጀብ!!

እኔማ ምን አሰብኩ መሰላችሁ? ጥምቀት ለምን ሁለቴ አይከበርም አልኩኝ (ግን ለራሴ ነው) (ከተማዋ እኮ አበባ መሰለች!) ጥምቀት እንዲህ ከሆነ ግን ለምንስ የፖለቲካ ጥምቀት፤ የዲሞክራሲ ጥምቀት፣ የልማት ጥምቀት፣ የመልካም አስተዳደር ጥምቀት፣ የጥበብ ጥምቀት፣ የፕሬስ ነፃነት ጥምቀት፣ የመድብለ ፓርቲ ስርአት ጥምቀት፣ ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል ጥምቀት ወዘተ… ወዘተ… አያሌ የህዳሴ ጥምቀቶችን አይኖሩንም ስልም ተመኘሁ - ሁሉም በአንድ መንፈስ ከልቡ የሚያከብረው፡፡ ባይገርማችሁ… በፕሮፓጋንዳ ያልተካበደ ህዳሴ እንዴት እንዳማረኝ አልነግራችሁም (አምሮት መብቴ መሰለኝ!) ውድ አንባቢያን፡- ፕሮፓጋንዳ ያልበዛበት ፖለቲካ የት እንደሚገኝ የምታውቁ ከሆነ ብትጠቁሙኝ ወሮታውን እከፍላለሁ፡፡ እኔ የምለው ግን… እኔ ብቻ ነኝ ወይስ እናንተም ናችሁ የፖለቲካ ህዳሴ የናፈቃችሁ? ለነገሩ ባይናፍቃችሁም አይፈረድባችሁም! (ተስፋ ቆርጣችሁ እኮ ነው!) እንዴ ፖለቲካችን “ከርሞ ጥጃ”፣ “ታጥቦ ጭቃ” ሲሆንባችሁስ? እውነቱን ልንገራችሁ አይደል… በጥንቱ አካሄድማ የፖለቲካ ህዳሴን መመኘት ባዶ ህልም ከመሆን ፈፅሞ አያልፍም፡፡ ለውጥ የምንሻ ከሆነ በብሄራዊ የእግር ኳስ ቡድናችን ላይ የምናየውና የምንሰማው አይነት አዲስ አቅጣጫና አካሄድ ልንከተል ግድ ይለናል፡፡በእርግጥ በአንድ ጀንበር ስር ነቀል ለውጥ መጠበቅ ሲበዛ የዋህነት ነው፡፡ እንኳንስ በጦቢያ ፖለቲካ ቀርቶ በየትም አገር ቢሆን ሁሉም ነገር ቀስ በቀስ እያደገ ነው የሚመጣው፡፡

የአፍሪካ ተቃዋሚዎች ስልጣንም ሆነ ዲሞክራሲ ዛሬውኑ ካልተንበሸበሽን ብለው የሙጥኝ ሲሉባቸው ፈረንጆቹ ምን እንደሚሉ ታውቃላችሁ? “ዲሞክራሲ ሂደት ነው!” ይሉና ይገላገሏቸዋል፡፡ እንዴ ምን ያድርጉ ታዲያ? ለነገሩ የእኛዎቹንም እኮ እናውቃቸዋለን… ምርጫን የሞት ሽረት ጉዳይ ያደርጉት የለም እንዴ! ለዚህ እኮ ነው የሥነልቦና ትምህርት የሚያስፈልጋቸው፡፡ ከምሬ ነው… ፖለቲከኞቻችን የAttitude ለውጥ ካላመጡ ፖለቲካው መቼም አይለወጥም! እኔማ የስነልቦና ብቻ ሳይሆን የፖለቲካ አሰልጣኝም (coach ወይም mentor ነገር) ይፈልጋሉ ባይ ነኝ! (ኢህአዴግንም ይጨምራል!) ፖለቲካ እኮ ብስለትም ብልህነትም ይፈልጋል፡፡ አጉል ብልጣብልጥነት ብቻውን የትም አላደረሰማ!! (ካላመናችሁኝ ኢህአዴግን ተመልከቱት!) ከችኩሉ ጥላቻ ተኮር ፖለቲካችን የምንላቀቀውም በጥሩ አሰልጣኝ ድጋፍ ይመስለኛል (የፖለቲካ ሰውነት ቢሻው ቢገኝማ ሽረት ነበር!) የሚገርማችሁ ግን በፖለቲካው ውስጥ ፀጉራቸው እስኪሸብት ኖረውበትም ዘንድሮም ቅንጣት ታህል ያልተለወጡ አያሌ ፖለቲከኞች በጦቢያ ምድር ሞልተው መትረፋቸው ነው፡፡ ልብ አድርጉ! እኔ ፈፅሞ የአገሬን ፖለቲከኞች የማንኳሰስ ድብቅ አጀንዳ የለኝም፡፡ የማንም ተላላኪም አይደለሁም! (ለምሳሌ የሻዕቢያ!) ራሳቸው ፖለቲከኞቻችን እኮ ራሳቸውን ለማንኳሰስ ማንንም አያክላቸውም!! (እዳ እኮ ነው የገባነው!) ባለፈው ሰሞን የኢንጂነር ሃይሉ ሻውል ፓርቲ የቀድሞ አመራሮች የቆየ ውዝግባቸወን እንደ አዲስ ሊጀምሩ መሆኑን ሰምቼ እንዴት እንደተቃጠልኩ አልነግራችሁም፡፡

እስቲ ይታያችሁ… ከኢህአዴግ ጋር የማይቀርላቸው “ልፍያ” ሳያንሳቸው እርስ በእርስ ፍልምያ መግጠማቸው ምን የሚሉት እዳ ነው (ወይስ የወዳጅነት ግጥምያ መሆኑ ነው!) እንዲህ ያሉት እኮ ፖለቲካም፣ ፓርቲም ወደሚለው ጉዳይ ከመግባታቸው በፊት ለራሳቸው ክብር መስጠትን የግድ መማር አለባቸው (እድሜማ አላስተማራቸውም!) ፈረንጆቹ postive attitude, self esteem ምናምን የሚለውን በደንብ በውስጣቸው ካሰረፁ በኋላ በማንኛውም ፈተናና ወከባ ተከበውም ቢሆን ፅናትና ብርታት ካላቸው ስኬት እንደሚቀዳጁም መማር፣ መሰልጠን፣ መለማመድ ያስፈልጋቸዋል፡፡ የምርጫ ሰሞን ወከባን ለማስቀረት ብልሃቱ ዝግጅት ብቻ ነው! ኢህአዴግ ከችግሩ (ኃጢያቱ) ነፃ ነው እያልኩ ግን እንዳይመስላችሁ፡፡ የችግሩ እናት ማን ሆነና! በነገራችሁ ላይ ለኢህአዴግ የሚሰጠው ስልጠና ማተኮር ያለበት… ጦቢያን ለማሳደግ፣ ለማበልፀግ፣ ከድህነት ለማውጣት፣ ዲሞክራሲን ለማስፈን ወዘተ ከላይ የተቀባሁት እኔና እኔ ብቻ ነኝ የሚለው ክፉኛ የተጣባው አመለካከቱ ላይ ነው፡፡ “ፀሃዩን ንጉስ” በመቃወም ወደ ትግል የገባ ፓርቲ እንዴት ያንኑ የተቃወመውን አመለካከት ያቀነቅናል? (ታሪክ ራሱን ይደግማል አሉ!) ይሄ ሁሉ ስጋት ከምን የመጣ እንደሆነ እንድታውቁልኝ እሻለሁ! አያችሁ… እስከዛሬ ኦክስፎርድ ዲክሽነሪ Famine የሚለውን ቃል Food Shortage, scarcity, starvation ወዘተ በማለት ከፈታ በኋላ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ምሳሌ የሚጠቅሰው ጦቢያን እንደነበር እናውቃለን አይደል! አሁን ደግሞ ሳናስበው “ኋላ ቀር ፖለቲካ” ለሚለውም ቃል ዳግም አገራችን በዲክሽነሪው ላይ እንዳትጠቀስና ዳግም ሼም በሼም እንዳንሆን ክፉኛ ሰግቻለሁ፡፡

እናላችሁ… አገሬን እወዳለሁ የሚል ዜጋ ሁሉ ጦቢያን ከኋላቀር ፖለቲካ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማውጣት ከፍተኛ እርብርቦሽ ያደርግ ዘንድ ጥሪ ቀርቦለታል፡፡ እኔ የምለው ግን… ሰሞኑን በድራማ መልክ በኢቴቪ የሚተላለፈውን ማስታወቂያ አይታችሁልኛል - በሁለት ጫማ የሚገዙ እንስቶች የተሰራውን ማለቴ ነው፡፡ በስተመጨረሻ ላይ አንደኛዋ አዲስ የገዛችው ጫማ ተረከዟን እንደላጣትና እግሯን እንዳቃጠላት ለጓደኛዋ በምሬት ስትነግራት “በደንብ ሳትመርጪ ለምን ገዛሽ?” ትላታለች (ዋጋሽን አገኘሽ በሚል ስሜት!) ለካስ ነገርዬው ለሚያዝያው የአዲስ አበባና አካባቢ ምርጫ የተሰራ ማስታወቂያ ነው፡፡ እኔ እኮ የቻይና ጫማ ገዝታ የተቃጠለች ነበር የመሰለኝ፡፡ (ቀላል ተሸወድኩ!) ለነገሩ የማይሆን ፓርቲ መምረጥ ከቻይና ጫማም የበለጠ ሊያቃጥል ይችላል፡፡ (ፈጣሪ ይጠብቀን እንጂ!) በመጨረሻ በምርጫው ለሚሳተፉ ፓርቲዎች (ከ29ኙ ውጭ) ሁሉ የሚመች ነጠላ ዜማ እንዳገኘሁላቸው ሳበስራቸው ኩራት ይሰማኛል (ቃል በቃል መቅዳት ያኮራል ተብሎ የለ!) እንዲህ የሚል ነው የዜማው ግጥም፡- በቃ በቃ አልፈልግም ሌላ ላይመች ላይደላ… (ከጫማው ማስታወቂያም ጋር ይሄዳል አይደል? በምርጫው የምትሳተፉ ፓርቲዎች ይመቻችሁ!!) ,