Administrator

Administrator

ከዕለታት አንድ ቀን ሁሉም የስሜት ዓይነቶች ይኖሩበት የነበረ አንድ ደሴት ነበረ ይባላል፡፡ እነዚህም ስሜቶች ደስታ፣ ሐዘን፣ ዕውቀት እንዲሁም ፍቅርን ጨምሮ በርካታ ሌሎች ነበሩ፡፡ አንድ ቀን ያ ደሴት ሊሰምጥ ነው የሚል ማስታወቂያ ተነገረ፡፡ ሁሉም በየፊናቸው ጀልባ እየሰሩ፣ ዘር ማንዘሮቻቸውን ይዘው፤ እግሬ - አውጪኝ እያሉ ከደሴቲቱ ወጡ፡፡ ከፍቅር በስተቀር፡፡ ፍቅር፤ “የመጣው ይምጣ እንጂ ስንት ዘመን የኖርኩበትን ደሴት ጥዬ አልሄድም” አለ፡፡ “የመጨረሻዋ ቅጽበት መጥታ ምርጫ ካላጣሁ በስተቀር ንቅንቅ አልልም” ሲል ወሰነ፡፡ ደሴቱ ሊሰጥም ተቃረበ፡፡ ፍቅር እርዳታ የሚያሻው ሰዓት ደረሰ፡፡

በአንድ ትልቅ ጀልባ ላይ ሆኖ ሀብት እየተኮፈሰ በፍቅር አጠገብ ሲያልፍ ታየ፡፡ ይሄኔ ፍቅር፤ “ሀብት ሆይ! ከአንተ ጋራ ልትወስደኝ ይቻልሃልን” አለና ጠየቀው፡፡ ሃብትም፤ “ወዳጄ ፍቅር! በጀልባዬ ላይ ስፍር ቁጥር የሌለው ብርና ወርቅ፣ ሌላም ጌጣጌጥ ስለከመርኩኝ፤ አንተን የማስቀምጥበት ቦታ የለኝም፡፡ ፍቅርም ሀብት እንደማይወስደው ሲያውቅ፤ ውብ በሆነች ጀልባ ላይ ኮርቶ ተቀምጦ እየፈሰሰ በአጠገቡ እያለፈ ወዳለው ወደ አያ ከንቱነት ሄዶ፤ “ከንቱነት ሆይ እባክህ ከዚህ ከሚሰምጠው ደሴት አውጥተህ ወደ ዳርቻው ውሰደኝ፤ እርዳኝ” አለው፡፡ “አዬ፤ አየህ አቶ ፍቅር አንተ ሁለመናህ እርጥብ ነው፡፡ ውብ ጀልባዬን ታረሰርስና ታቆሽሽብኛለህ፡፡ ስለዚህ አልጭንህም” ሲል ይመልሳል፡፡ ቀጥሎ ፍቅር በአካባቢው ወደነበረው ወደ አቶ ሐዘን ሄደና፤ “አብሬህ እሄድ ዘንድ ፍቀድልኝ” አለና ተማፀነው፡፡

“አይ አቶ ፍቅር፤ በጣም አዝናለሁ፡፡ እኔ አሁን ብቻዬን መሆን ያለብኝ ሰዓት ነው” ቀጥሎ በፍቅር አጠገብ የምናልፈው ደስታ ነበረችና ወደሱዋ ተጣራ፡፡ ደስታ ግን በጣም ፍንድቅድቅ ብላ ስለነበር የፍቅርን ድምጽም ለመስማት ሳትችል አልፋው ሄደች፡፡ በዚህ መካከል አንድ ድንገተኛ ድምጽ ተሰማ፡፡ “ፍቅር ሆይ፤ ና ወደኔ እኔ እወስድሃለሁ” አለ፤ ያ የአንጋፋዋ እመቤት ድምጽ፡፡ ፍቅር ይህን የተባረከ ዕድል በማግኘቱ እጅግ ሀሴት ተሰምቶት ወዴት እንደሚሄዱ እንኳ ለመጠየቅ ጊዜ አልወሰደም፡፡ ወደ አንድ ደረቅ ምድር በደረሱ ጊዜ አንጋፋዋ እመቤት ወደራስዋ አቅጣጫ ተጓዘች፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ፍቅር ወደ አንጋፋው ዕውቀት ሄደና፤ “አሁን እርዳታ ያደረገችልኝ አንጋፋ እመቤት ማን ናት?” ሲል ጠየቀው፡፡ ዕውቀትም፤ “ጊዜ ናት” ሲል መለሰ፡፡

“ጊዜ? ጊዜ ለምን ትረዳኛለች” አለና በአግራሞት ጠየቀ፡፡ ዕውቀትም ጥልቅ ጥበባዊ ፈገግታ ፈገግ ብሎ፤ “ፍቅር ምን ያህል ዋጋ እንዳለው የሚያውቅ ዕውቀት ብቻ ነው” ሲል መለሰ፡፡ *** በወርሃ የካቲት ፍቅር፣ ዕውቀትና ጊዜ አይንሳን፡፡ ለውጥ ምን ጊዜም አይቀሬ ነው፡፡ ከሚሰምጥ ደሴት ግን ያውጣን፡፡ ዱሮ ስናውቀው በ60ዎቹ የየካቲት ወር ብዙ ነገር አርግዞ ነበር፡፡ የዛሬ አርባ ዓመት ግድም የለውጥ ንፋስ በየአቅጣጫው ወጀቡን ይዞ መምጣቱ ይታወሰናል፡፡ የሁሉም መሽከርክሪት የሥርዓት ለውጥ ነበር፡፡ የቤንዚን ዋጋ መናር፣ ከዚያ የተያያዘው የታክሲዎች ሥራ ማቆም፣ የወሎ ረሃብ፣ የተማሪዎች እንቅስቃሴ የመምህራን ሥራ ማቆም፣ የወታደሮች የደሞዝ ጭማሪ ጥያቄ፣ የሙስሊሙ ህብረተሰብ የሃይማኖት እኩልነት ጥያቄ፣ ወዘተ ብርቱ የለውጥ ጥንስስ ሆነው ከተፍ ያሉት በወርሃ የካቲት ነበር፡፡ ጠቅለል አድርገን ስናነጥራቸው የኢኮኖሚ ጥያቄና የፖለቲካዊ አስተዳደር በደል ጥያቄዎችና የሃይማኖት እኩልነት ጥያቄዎች ግዘፍ - ነስተው እናገኛቸዋለን፡፡ ያኔ የአለም አቀፉ ፖለቲካ ባጠቃላይ ሲታይ ሁለት ጐራዎች ነበሩት፡፡

ስለሆነም ማናቸውም አገር የውስጥ ችግሩን ለመፍታት የውጪ እጅ ካስፈለገው ወደነዚህ ሁለት ጐራዎች ያንጋጥጣል፡፡ ያኔ ያላደጉት አገሮች ቻይና፣ ህንድ፣ አፍሪካ እና ላቲን አሜሪካ ነበሩ፡፡ አንጋፎቹ ጐራዎችም ቋታቸውን የሚሞሉት የነዚህኑ ያላደጉ አገሮች ድንግል አንጡራ ሀብት በመቦጥቦጥ ነበር፡፡ ዘመን ተሻረ፤ ሁኔታዎች ተለዋወጡ፡፡ የምዕራቡ ኃይል ብቸኛ ጐራ ሲሆን ሌሎቹ ምዕራብ ያልሆነው ክፍል ተቃራኒ ጐራ ናቸው፡፡ እነቻይናና ህንድ ወደላይ ወጡ፤ ያደጉ አገሮች ሆኑ፡፡ ላቲኖችም ወደላይ ተጓዙ፡፡ ባለበት የሚረግጡትና ቆሞ ቀር የሆኑት ከሞላ ጐደል የአፍሪካ አገሮች ናቸው፡፡ ስለዚህ ዛሬም ለውጥ ለማምጣት ጠረጴዛ ዙሪያና ምርጫን ለመንተራስ ቢፍጨረጨሩም ገና ከጫካ አልወጡም፡፡ ጠመንጃ ከመንከስ አልተላለቁም፡፡ ከጐሣ ግጭት አልወጡም፡፡

የበሽታ መናኸሪያ የጉስቁልና መፈልፈያ ከመሆን ገና አልዳኑም፡፡ የዱሮዎቹ ትውልዶች ጭቆናን ለመቃወም፣ ግፍን ለመጋፋትና የውስጥ ታጋዮቹ ብዝበዛን ለመታገል ቆርጠው ይነሱ ነበር፡፡ ለውስጥ ታጋዮቹ ዓለም አቀፋዊ ኃይሎችም ያግዟቸው ነበር፡፡ ዛሬ ያ የለም፡፡ ሆኖም የማይለወጥ ነገር የለም፡፡ ሁሉም ነገር ይለወጣል፤ ከለውጥ ህግ በስተቀር (Everything changes except the law of change እንዲል ፈረንጅ) ሀገራችንም ከለውጡ ሽታ መጋራቷ አይቀሬ ነው፡፡ ቢያንስ “የመሬት ላራሹ” ጥያቄን ምላሽ ማግኘት ማስታወስ ከቻልን ወርሃ የካቲትን ልናሰምርበት እንችላለን፡፡ ያልተመለሱ ጥያቄዎችን ዛሬም አጽንኦት መስጠት አስፈላጊ ነው - ዲሞክራሲው ሀቀኛ መሆን አለበት፡፡ የኢኮኖሚ ብዝበዛ ተቋማዊም ሆነ ድርጅታዊ፤ አሊያም ግለሰባዊ ዛሬም በፅኑ ልንዋጋው ይገባናል፡፡

ከውጪ ኃይሎች በማናቸውም መልክ የሚመጣውን አሉታዊ ተጽእኖ ዐይናችንን ከፍተን ወገባችንን አጥብቀን መቋቋም አለብን፡፡ የሃይማኖት ችግር የራሳችን ይሁን የውጪ ኃይሎች ፍላጐት ብለን አጥርተን ማሰብ አለብን፡፡ የፍትሕና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ በተግባር መመለስ አለበት፡፡ ህዝብ እየለፋ እየታተረ የሚገነባውን ኢኮኖሚ የባለጊዜ ልጅ ልጆች የሚንዱ ከሆነ “እኔ እያለቀስኩ እሸምታለሁ፣ እሷ እየዘፈነች ትፈጫለች” ይሆናል፡፡

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የተቋቋመበት ሃምሳኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ በተለያዩ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶች እንደሚከበር የበዓሉ አዘጋጅ ብሔራዊ ኮሚቴ አስታወቀ፡፡
ከመንግሥት ኮሙኒኬሽን ፅህፈት ቤትና ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተዋቀረው ብሔራዊ ኮሚቴ አባላት የዛሬ ሳምንት በአምቦ ከተማ በተዘጋጀ አውደ ጥናት ላይ እንደተገለፀው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የተመሰረተበት ዋነኛ እለት ግንቦት 17 የሚከበር ሲሆን ከዚያ በፊት እና በኋላ የተለያዩ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶች ይቀርባሉ፡፡ “ፓን አፍሪካኒዝምና የአፍሪካ ሕዳሴ” በሚል መሪ ቃል በሚከበረው የወርቅ ኢዮቤልዩ፤ ታዋቂ ድምፃውያን እና እግር ኳስ ተጨዋቾች ወደ አዲስ አበባ ተጋብዘው ከአድናቂዎቻቸው ጋር ይገናኛሉ፡፡
በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ጥናታዊ ፊልም የሚቀርብ ሲሆን የምስረታውን ጉዞ የተመለከቱ ቴምብሮችም ይታተማሉ ተብሏል፡፡ ከስምንት ሳምንት በላይ የሚቆይ የአማርኛና እንግሊዝኛ ጥያቄና መልስ ውድድር ከታሚሶል ኮሙኒኬሽን ጋር በመተባበር እንደሚዘጋጅም ታውቋል፡፡

በተለያዩ የኪነጥበባት ዘርፎች የተሰማሩ አርቲስቶች ለ “መቄደንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል” ገቢ ማሰባሰቢያ ነገ በዘጠኝ ሰዓት የእግር ጉዞ እንደሚያደርጉ ተገለፀ፡፡ በዝግጅቱ ላይ ከአርቲስቶች በተጨማሪ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ አርበኞች እና ሰላሳ ሺህ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች የእግር ጉዞው በሚጀመርበት የኤግዚብሽን ማዕከል ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
መቄዶንያ ኮተቤ አካባቢ በሚገኘው መጠለያው 150 አረጋውያንና የአእምሮ ህሙማንን ያለምንም የውጪ የገንዘብ ድጋፍ የሚረዳ ድርጅት ነው፡፡

ኩል ፊልም ፕሮዳክሽን “አምራን” የተሰኘ አስቂኝ የፍቅር ፊልም ነገ በአዲስ አበባ የግል ሲኒማ ቤቶች እንደሚያስመርቅ አስታወቀ፡፡ በፊልሙ ላይ ማህደር አሰፋ፣ ሳምሶን ታደሰ፣ ሠለሞን ሙሄ፣ ሰላም አሰፋ እና አሸናፊ ከበደ ተውነውበታል፡፡
የ103 ደቂቃ ርዝመት ያለውን ይሄን ፊልም ሰርቶ ለማጠናቀቅ ስምንት ወራት ፈጅቷል፡፡ በብሌን ሚዲያ ፕሮዳክሽን የተዘጋጀው “ፍቅር በአጋጣሚ” የተሰኘ የ100 ደቂቃ ፊልም ነገ እንደሚመረቅ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ አዝናኛ የፍቅር ፊልሙን ለመስራት አስራአራት ወራት የፈጀ ሲሆን በፊልሙ ላይ ሩታ መንግሥተአብ፣ ዮናስ አሰፋ፣ ዳንኤል ገበየሁ፣ መቅደስ መለስ፣ ሲያምረኝ ተሾመ እና ሌሎችም ተውነዋል፡፡

 

ሚዩዚክ ሜይዴይ በገጣሚ አያልነህ ሙላቱ “ከድጡ ወደ ማጡ” የግጥም መፅሐፍ ላይ ነገ ከቀኑ ስምንት ሰዓት ጀምሮ በብሄራዊ ቤተመዘክር ውይይት እንደሚያደርግ አስታወቀ፡፡
“የመግቢያና የይዘት ተቃርኖ” በሚል ርእስ የሚደረገውን ውይይት የሚመሩት ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ ናቸው፡፡

 

“ቪዚት ቱ ኢትዮጵያ” በተባለ ድርጅት ዘንድሮ ለሁለተኛ ጊዜ የታተመው የኢትዮጵያ ቱሪዝም ዳይሬክተሪ በአራት አህጉራት በሚገኙ 78 ሀገራት እንደሚሰራጭ ታወቀ፡፡ የድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ ቴዎድሮስ መርአዊ ስጦት ለአዲስ አድማስ ሲናገሩ፤ ዳይሬክተሪው ስድስት በዩኔስኮ ለመመዝገብ የታጩ የኢትዮጵያ ቅርሶችንና ታላቁ ሩጫን እንደ ቅርስ ማካተቱ ልዩ እንደሚያደርገው ጠቁመዋል፡፡ ዳይሬክተሪው በተጨማሪም በዓለም የተመዘገቡ ዘጠኝ ቅርሶችና የኢትዮጵያን ብሔራዊ ፓርኮች የያዘ መረጃ እንዳካተተ የታወቀ ሲሆን በነፃ የሚታደል 10ሺህ ቅጂ እንደተዘጋጀም ለማወቅ ተችሏል፡፡

በቁጥር አንድ መፅሐፉ የህወሐትን የትጥቅ ትግል ታጋዮችን ታሪክ በትግርኛ ያሳተመው ጋዜጠኛና ደራሲ ኃይላይ ሃድጉ፤ “ጽንአት ቁጥር 2” መፅሐፉን ከትናንት ወዲያ ከሰአት በኋላ በአዲስ አበባ ሂልተን አስመረቀ፡፡ በትግል ስሙ “ቃል (አል) አሚን” ተብሎ በሚጠራው ታጋይ የኋላእሸት ገብረመድህን ላይ ያተኮረውና በፎቶግራፎች የተደገፈው ባለ 320 ገፅ መፅሐፍ ሲመረቅ የህወሓት ነባር ታጋይ አቶ አባይ ፀሐዬ በክብር እንግድነት ተገኝተዋል፡፡ መፅሐፉን አንብበው አስተያየት ከሰጡት መካከል፤ የኢሠፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ ፖሊት ቢሮ ተለዋጭ አባል እና የቀድሞ መንግሥት ከፍተኛ ባለስልጣን አቶ ፋሲካ ሲደልል እንዲሁም የኢህአፓ እና የኢዲዩ አባላት ይገኙበታል፡፡ መፅሐፉ በ70 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

“በህዝብ ጥያቄ የተደገመ…” የሚሉት ነገር ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ ማንበብ፡፡ ሁልጊዜ ግርም የሚለው ነገር ምን መሰላችሁ… እኛ በቅርበትም በርቀትም የምናውቃቸው ሰዎች አንዳቸውም “ጥያቄ አቅራቢዎች ውስጥ አለሁበት…” ሲሉ አለመስማታችን፡፡ እኔ ይሄኔ…በቃ…“የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ እየተነበበ ነው” እንላለን፡፡ (ጥያቄ አለን…“አህዛብ እንጂ ህዝብ አይደላችሁም” ካልተባልን በስተቀር እንዴት ነው “እንዲደገም…” የሚጠይቁት ውስጥ የማንገባሳ! ቂ…ቂ…ቂ…)

እንዴት ሰነበታችሁሳ!

ሰውየው… የከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አስተማሪ ነው፡፡ እናላችሁ… ተማሪዎቹን ስለ ውሸት ሊያስተምራቸው ይፈልጋል፡፡ ትምህርቱን ለመጀመርም እንዲያነቡ የሰጣቸውን መጽሐፍ ከፍ ያደርግና “እዚህ መጽሐፍ ላይ ሀያ አምስተኛውን ምዕራፍ ያነበባችሁ ስንት ናችሁ?” ሲል ይጠይቃቸዋል፡፡ ክፍሉ ውስጥ ያሉ ሁሉ እጃቸውን ያነሳሉ፡፡
አስተማሪውም ምን ቢላቸው ጥሩ ነው…“ሥራዬ ከባድ ይሆናል ማለት ነው፡ መጽሐፉ ውስጥ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ የለም፡፡”
እናላችሁ…እንዲሀ አይነት የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ነው፡፡ ሰዎች ብቻ ሳንሆን ‘የሰማይ ስባሪ’ የሚያካክሉ ተቋማት፣ ‘የሰማይ ስባሪ’ የሚያካክሉ ‘ፐርሰናሊቲስ’…ምን አለፋችሁ…ከዳር ዳር የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አነበብኩ…” ማለት በጋራ የተሰጠን ባህሪይ እየመሰለብን ነው፡፡
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ፣ “ለምንድነው ህብረተሰባችን ውስጥ እንዲህ መተማመን የጠፋው?” ብላችሁ ጠይቃችሁ አታውቁም፡፡ እንደዚህ አይነት ህብረተሰብን ከስረ መሰረቱ ሊነቅሉ የሚችሉ ነገሮችን ጥናት አካሂዶ መፍትሄ የሚጠቁመን ይጥፋ! የምር አስቸጋሪ ነገር ነው፡፡ ያለመተማመን የግለሰቦች፣ የቡድኖች ምናምን ጉዳይ ብቻ መሆኑ ቀርቶ ወደ አገር ደረጃ ከፍ ሲል አሪፍ አይደለም፡፡ በብዙ ነገር “በእነሱ ቤት እኮ እኛን ማታለላቸው ነው!” እየተባባልን ነው፡፡
እንዲህ የሆንነው ለምን መሰላችሁ…የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ስለሄድን፡፡
ለምሳሌ መግለጫዎች ምናምን ስንሰማ ወይም ስናነብ “እሱን እንኳን ተዉት፣ ምን ያላልንበት ዳገት የለም አለች እንስሳዋ…” ምናምን ማለት ከጀመርን ውለን አደርን፡፡ አሀ..ልክ ነዋ…ብዙ ነገሮች ከቃላተ ጋጋታና ከ‘ዘመኑ አማርኛ’ ባለፈ ከመግለጫው አዳራሽ እንደተዋጣ ሁሉም ነገር ‘የሀላፊ ጊዜ ግስ’ ሆኖ ይቀራላ!
በተበለጨለጨ አዳራሽ ‘የተብለጨለጩ መገለጫዎች’ ሲሰጡን ለማመን እየተቸገርን ያለነው የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ነው፡፡
(በዚህ መሀል የሚያሳዝነው ምን መሰላችሁ… ‘እውነት ሊሆኑ የሚችሉ’ ነገሮች ሜዳ ላይ እየቀሩ መሆናቸው፡፡)
ለምሳሌ…ይሄ “በህዝብ ጥያቄ የተደገመ…” የሚሉት ነገር ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ ማንበብ፡፡ ሁልጊዜ ግርም የሚለው ነገር ምን መሰላችሁ… እኛ በቅርበትም በርቀትም የምናውቃቸው ሰዎች አንዳቸውም “ጥያቄ አቅራቢዎች ውስጥ አለሁበት…” ሲሉ አለመስማታችን፡፡ እኔ ይሄኔ…በቃ…“የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ እየተነበበ ነው” እንላለን፡፡ (ጥያቄ አለን…“አህዛብ እንጂ ህዝብ አይደላችሁም” ካልተባልን በስተቀር እንዴት ነው “እንዲደገም…” የሚጠይቁት ውስጥ የማንገባሳ! ቂ…ቂ…ቂ…)
እናላችሁ…የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ነው፡፡
አንዳንዴ ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…ይሄ “በህዝብ ጥያቄ የተደገመ…” ዝም ብሎ ምክንያት መፍጠሪያ አይነት ነገር ይመስለኛል፡፡ “ይህ ፕሮግራም ጠቃሚ ነገሮች ስላሉበት ያዩት እንዲደግሙት፣ ያላዩት እንዲያዩት ተደግሟል…” ማለት ይቻላል፡፡ ለዚህ እኮ ‘ዋር ኤንድ ፒስ’ ‘ክራይም ኤንድ ፐኒሽመንት’ ምናምን መዘርዘር አያስፈልግም፡፡
እናላችሁ…የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ነው፡፡
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል… እዚህ አገር አዲስ አሠራር ሁሉ ሳይሳካ በሌላ አዲስ አሠራር ለምን የሚተካ ይመስለኛል መሰላችሁ…ገና የወጡ ‘ናሙና’ ሳይቀመስ እምቢልታና መለከቱ ስለሚበዛ!
ለምሳሌ አንዳንድ ሰው በአጭር ጊዜ መልኩ ምናምን ተለዋውጦ ስናየው “የእግዚአብሔር ሥራ ነው…” ምናምን ቢለን ምንም አናምነውም፡፡ እዚህ አገር አፍንጫ፣ ‘ብሬስት ምናምን’ አይነት ‘ፕላስቲክ ሰርጀሪ’ ተለምዷላ!
መልክን የመለወጥ ነገርን ካነሳን አይቀር…ይቺን የሆነ ቦታ ያነበብኳትን ነገር ስሙኝማ…የሆነች መካከለኛ ዕድሜ ላይ የደረሰች ሰው የልብ ድካም ይገጥማትና ሆስፒታል ትሄዳለች፡፡ እናላችሁ… እየታከመች ሳለች በመንፈሷ እግዚአብሔር ይታያታል፡፡ ይሄኔ እያስተዛዘነች “አምላኬ፣ በቃ አለቀልኝ ማለት ነው?” ትለዋለች፡፡ እሱም፣ “አይ ያንቺ ጊዜ ገና ነው፡ ምድር ላይ ገና 43 ዓመት፣ ከ2 ወር ከ8 ቀን ይቀርሻል” ይላታል፡፡ሲሻላትም ራሷን ለመለወጥ ‘ፕላስቲክ ሰርጀሪ’ ለማድረግ ሀኪም ቤት ትሄዳለች፡፡ አፍንጫዋ ሰልካካ ተደረገ፣ ሾል ያለ አገጯ ተስተካከለ፣ ‘ብሬስቶቿ’ ሞላ እንዲሉ ተደረጉ፣ የጸጉሯ ቀለም ተለወጠ…ብቻ ሙሉ ለሙሉ ሌላ ሰው ሆነች፡፡ ህክምናው አልቆ ልክ ከሆስፒታሉ ስትወጣ ግን መኪና ይገጫትና ትሞታለች፡፡
ከዛም እግዜሐር ፊት ስትቀርብ ምን ትላለች…“ገና አርባ ሦስት ዓመት አለሽ አላልከኝም ነበር እንዴ! ለምንድነው ከመኪናው ፊት ስበህ ያላወጣኸኝ?” ትለዋለች፡፡ እግዜሐር ምን ብሎ ቢመልስላት ጥሩ ነው… “ሙሉ ለሙሉ ተለውጠሻል፣ አንቺ መሆንሽን አላወቅሁማ!” አላት፡፡
እናማ… ይሄ ሙሉ ለሙሉ ለመለወጥ የሚደረገው ጥረት አበሳም አለው ለማለት ነው፡፡ ነገራችን ሁሉ ድንብርብሩ እየወጣ እንደገና የውሸት አፍንጫና አገጭ እየበዛ ሲሄድ “የእግዚአብሔር ሥራ…” የሆነውን ሁሉ እየተጠራጠርን ነው፡፡እናላችሁ…የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ያለመተማመን የባህሪያችን ዋና መገለጫ እየሆነ ነው፡፡
እኔ የምለው…መቼም የዘንድሮ ነገራችን ቢወራ፣ ቢወራ ፈቀቅ የማይል ሆኗል፡፡ በብዙ ነገሮች በአለባባስ በሉት፣ ከሰዎች ጋር ሰላምታ በመለዋወጥ በሉት፣ በምግብ ‘አመራራጥ’ በሉት…እዚቹ እኛዋ ሀበሻ አገር ሆኖ የፈረንጅነት የክብር ዜግነት አለኝ ሊል ምንም የማይቀረው የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የሚል መአት አለላችሁ፡፡
ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…የዜግነት ነገር ካነሳን አይቀር ይቺን ስሙኝማ፡፡ ሩሲያዊው፣ ፈረንሣዊውና እንግሊዛዊው አዳም የምን አገር ዜጋ እንደሆነ ይከራከሩ ነበር፡፡ፈረንሣዊው፣ “ያለምንም ጥርጥር አዳም ፈረንሣዊ ነው፡፡ ከኢቭ ጋር እንዴት በስሜት ፍቅር እንደሚሠራ አታዩትም!” አለ፡፡እንግሊዛዊው ደግሞ፣ “የነበረቻቸውን ብቸኛ አፕል ለሴቷ ሰጣት፡ በእርግጥም እንግሊዛዊ እንጂ የሌላ አገር ዜጋ ሊሆን አይችልም፣” ይላል፡፡
ሩስያዊው ይህን ሁሉ ከሰማ በኋላ ምን ቢል ጥሩ ነው…“አዳም የሌላ አገር ዜጋ ሳይሆን ሩስያዊ ብቻ ነው ሊሆን የሚችለው፡፡ ከአንዲት አፕል ሌላ ምንም ሳይኖራቸውና ራቁቱን ወዲህ ወዲያ እያለ ብርድ እየቀፈቀፈው መንግሥተ ሰማያት ነኝ ብሎ የሚያስብ ሩስያዊ ብቻ ነው፡፡” አሪፍ አይደለች!
“አንድ ቁራሽ ዳቦ እንክት ያደርግና
አንድ ጣሳ ውሀ ግጥም ያደርግና
ተመስገን ይለዋል ኑሮ ተባለና…” የምንለው አይነት የእኛ አገር ጉድ እንደ ማለት ነው፡፡
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…የሩስያን ነገር ካነሳን ይቺን የተስማማችኝን ቀልድ ስሙኝማ…ስታሊን ይሞትና ገሀነም ይወርዳል፡፡ እሱ እዛ በወረደ በጥቂት ቀናት ውስጥ አንድ ሌሊት መንግሥተ ሰማያት በር ላይ ቅልጥ ያለ ጩኸት ይሰማል፡፡ ለሽ ያለ እንቅልፍ ላይ የነበሩት መላዕክት ተደናግጠው ይነቃሉ፡፡ ቅዱስ ዼጥሮስ በሩን ሲከፍት ደጅ የሰይጣን መአት ሜዳውን ጥምቀተ ባህር አስመስሎታል፡፡ “ምን ሆናችሁ! ደግሞ እዚሀ ምን ልትሠሩ መጣችሁ?” ይላቸዋል፡ እነሱም “እኛን ከገሀነም እንደመጣን የመጀመሪያዎቹ ስደተኞች ቁጠረን፣ የፖለቲካ ጥገኝነት ይሰጠን፣” ይሉታል፡፡ እሱም ምክንያታቸውን ሲጠይቃቸው ምን ቢሉት ጥሩ ነው… “ስታሊን የሚባል ሰው መጥቶ ገሀነምን በአንድ እግሯ አቁሟታል፣ የእሱን ጭቆና መቋቋም ስላልቻልን በመንግሥተ ሰማያት ጥግኝነት ይሰጠን” አሉ ይባላል፡፡እናላችሁ…የግብረ ገብ ጉዳይ ያገባናል ማለት የሚገባቸው አንዳንድ ተቋማት… እንኳን እኛን ወደ ትክክለኛ አቅጣጫ መመለስ ቀርቶ…አለ አይደል… ለራሳቸውም ‘ራዳሩ ሲጠፋባቸው/ሲያገኙ፣ ሲጠፋባቸው/ሲያገኙ’…አንዳንዴ ራሳቸው አቅጣጫ የሚያሳይ ያጡ ይመስላል፡፡ ረናማ…አሌ የሚለን እየጠፋ የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ነው፡፡
መልካሙን ያምጣልንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

“እግዚአብሔር የፈቀደውን
ነው የምንሰራው”ብፁዕ አቡነ ማትያስ

“ከኔ ይበልጥ ወንድሞቼ
እንዲመረጡልኝ ነው የምመኘው”
(ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ፤ የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ)

“ፓትርያሪክም ብሆን ሊቀጳጳስ እርቁ ይቀጥላል
(ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ፤ የሰሜን ጐንደር ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ)
ለስድስተኛ ፓትርያርክነት እጩ መሆንዎን የሰሙት ከማን ነው?
ሰው ዝም ብሎ ያወራል፡፡ እገሌ ይሆናል ይባላል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት እጩ ነህና እንድትመጣ አሉኝ፡፡ አሁን ባለፈው የካቲት 13 ነው አዲስ አበባ የገባሁት፡፡ እኔ ምንም የማውቀው ነገር የለም፤ ከኢየሩሳሌም ተነስቼ ስገባ የፓትርያሪክ ምርጫ ሕግ ተረቋል ተባለ፡፡ ያ ሕግ ታህሳስ 30 ለሲኖዶስ ይቀርባልና በሲኖዶስ አባልነትህ ና ተባልኩ፤ ሥራ ይበዛ ስለነበር አልተመቸኝም፡፡ ጥር 6 ቀንም ለሌላ ስብሰባ ና ተብዬ አልቻልኩም፡፡
ቀደም ሲል የአሜሪካ ዜግነት እንደነበርዎ ሰምቻለሁ…አሁንስ?
በፈረንጅ አቆጣጠር ከ1994-1995 ዓም ችግር ስለነበረብኝ የአሜሪካ ፓስፖርት ይዤ ነበር፡፡ አሁን ግን ተለውጧል፡፡ ይኼ ከአሁኑ ምርጫ ጋር አይያያዝም፡፡ ለምርጫው ብዬ ፓስፖርት አልቀየርኩም፡፡ በመሰረቱ የኢየሩሳሌም ሊቀጳጳስ ሆኜ ከተመደብኩ በኋላ ሃሳቤ ወደ ኢትዮጵያዊነቱ ለመለወጥ ነበረ ተጓቶ ነው እንጂ፡፡ እንደዚህ አይነት እጬ እሆናለሁ ብዬ አላሰብኩም፡፡
ግን እንዴት የአሜሪካ ዜግነት ወሰዱ?
አይ እሱማ ---- የኢየሩሳሌም ሊቀጳጳስ በነበርኩበት ጊዜ የደርግ ወታደራዊ መንግሥት ተፅእኖ ነበረብኝ፡፡ መንግስት ደህንነቶች ከተሳላሚዎች ጋር እየላከ ብዙ ችግር አስከትሎብኛል፡፡ በዚያ ምክንያት ወደአሜሪካ ተሰደድኩ፡፡ እዚያ የነበሩትን ምዕመናንም ሳገለግል ቆየሁ፡፡ በኋላ ሲኖዶሱ ጠርቶ የአሜሪካ ሊቀጳጳስነቱን አፀደቀልኝ፡፡
በወቅቱ ፓትርያሪክ ተወግዘው ነበር-----
መወገዙማ የመጣው እኔ ደርግን ስላወገዝኩ ነበር፡፡ ደርግን ሳወግዝ የነበሩት ሰዎች እንዴት መንግሥትን ያወግዛል ብለው ፓትርያሪኩን አሳሳቱና አውግዘውኝ ነበረ፡፡
በኋላ ስመጣ በስህተት ነው ተብሎ አነሱት፡፡ የተወገዝኩት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለኃይማኖት ጊዜ ነው፡፡ የተነሳው ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሪዎስም ለቀው አቡነ ያዕቆብ አቃቤ መንበር በነበሩ ጊዜ ነው፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከመሾማቸው ጥቂት ጊዜ በፊት ነው ይሄ፡፡
ከአቡነ ጳውሎስ ጋርም ለፓትርያሪክነት ተወዳድረው ነበር ይባላል…
እኔ አወዳድሩኝ ብዬ አላውቅም፤ አሁንም ድሮም፡፡ ብቻ ከየክልሉ ሁለት ሁለት ተወዳዳሪዎች ሲባል ከአቡነ ጳውሎስ ጋር እኔ ሳላውቅ ተወዳድሬ እሳቸው ከአምስቶቹ እጩ ፓትርያሪኮች አንዱ ሆኑ፤እኔ ቀረሁ፡፡
ጠርተውኝ የመጣሁት ግን የመርቆሪዎስ ምክትል በነበሩት በብፁዕ አቡነ ዜና ማርቆስ ጊዜ ነበር፡፡ መወገዜን እኔም አላውቅም ነበር፡፡ ምን ሆኜ? ስል እንዲህ ተላልፎብህ ተባልኩኝ፡፡
ብፁዕነትዎ ሲወገዙ ሌላ አቡነ ማትያስ መሾማቸው ትክክል ነበር?
በቤተክርስትያን ባህላችን ሁለት ጳጳሳት በአንድ ስም አይጠሩም፡፡ ግን ያን ጊዜ ተደረገ፡፡ በአቡነ ተክለኃይማኖት ላይ ግፊት አድርገው ነው፡፡ ሆነ ብለው የእኔን ስም ለመውሰድ ያደረጉት ነው፡፡ ስመለስ ግን ፀፀት ውስጥ ገቡ፡፡
ብፁዕነትዎ ፓትርያሪክ ቢሆኑ እርቀ ሰላሙ በምን መልክ ይቀጥላል?
እርቀሰላሙ እንደሚቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ተናግሯል በዚያው መሰረት ይቀጥላል፡፡ ከሲኖዶስ የተለየ ሃሳብ ሊኖረኝ አይችልም፡፡
በፓትርያሪክነት ቢሾሙ በኢየሩሳሌም የቤተክርስትያኒቱን ይዞታ ለማስመለስ ምን ለመስራት አቅደዋል?
ፓትርያሪክ የመሆን ጉዳይ ሳይሆን እኔም ሆንኩ ሌሎቹ እንዲገፉበት ቅዱስ ሲኖዶሱን እገፋፋለሁ ከሆንኩ አለሁ ማለት ነው፡፡ ካልሆንኩ ደግሞ ቅዱስ ሲኖዶሱ ሥራዬ ብሎ ከግብፅ ኦርቶዶክስ ጋር ተነጋግሮ አንድ መፍትሄ እንዲገኝ ጥረት ይደረጋል፡፡ ወደ ሌላ ሀገረ ስብከት ብቀየርም ይሄ ይቀጥላል፡፡
ፓትርያርክ ቢሆኑ ከአምስተኛ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ምን የተለየ ነገር ይሰራሉ?
መቼም እግዚአብሔር የፈቀደውን ነው የምንሰራው፡፡ ቤተክርስትያኒቱ ትክክለኛውንና ቀጥተኛውን መንገድ አንድትይዝ፣ በውስጧ ያለው ሁሉ መንፈሳዊነትን የተጐናፀፈ እውነተኛነትን የተከተለ መሆን አለበት ባይ ነኝ፡፡ በተቻለ መጠን ይህንን ወደ እውነተኛው መንገድ ለመመለስ ነው ተስፋ የማደርገው፡፡
ከአቡነ ጳውሎስ ስራዎች በጣም የሚያደንቁት ምንድነው?
ቅዱስነታቸው ዓለም አቀፍ ሰው ነበሩ፡፡ በዚህም ቤተክርስትያኒቱን አስተዋውቀዋል፡፡ በመንበረ ፓትርያርክ ግቢ ለጳጳሳት ማረፊያ አሰርተዋል፡፡
ቤት አልነበረም፡፡ መሰብሰቢያ አዳራሽ አልነበረም፣ ቤተመፃህፍት አልነበረም፡፡ እነዚህ ሁለቱን አደንቅላቸዋለሁ፡፡
መሻሻል ይገባቸዋል በሚሏቸው ጉዳዮች ላይ ለአቡነ ጳውሎስ አስተያየት አቅርበው ያውቃሉ?
አንዳንድ ስህተቶች ሳይ እነግራቸው ነበር፡፡ ለምሳሌ በስብከተ ወንጌል፣ በኃይማኖት አጠባበቅ በኩል የኃይማኖቱን ሥርዓት ያልጠበቁ ሰባኪዎች… በዘፈቀደ ሲሆን እናገራለሁ፡፡
ይቀበሉዎት ነበር?
ይቀበሉኛል ግን ነገሩ ከባድ ይሆንና የተባለው መቶ በመቶ ላይሰራ ይችላል፡፡ መቻቻል ጥሩ ነገር ይመስለኛል መቻቻል ከሌለ ሁከት ነው ያለው፣ የሕዝቡንና የሀገር አንድነት ለማስጠበቅ ተቻችሎ መስራት ያስፈልጋል፡ሌላ ምርጫ የለም፡፡ አንዱ ሌላውን ሳይቀማ መኖር መቻል አለበት፡፡


===============
በፓትርያርክነት ቢመረጡ ምን ለመሥራት አቅደዋል?
እግዚአብሔር አምላክ ለዚያ ካደረሰኝ ከዚያ በኋላ ነው የምናገረው፡፡
ነገር ግን እኔ የምመኘው ከአራቶቹ እጩዎች መካከል ለሀገር ለወገን ለቤተክርስትያን የሚያስብ አባት እግዚአብሔር እንዲሰጠን ነው፡፡ ለዚህም እግዚአብሔርን በፀሎት እጠይቃለሁ፡፡ ቅድሚያ ከኔ ይበልጥ ወንድሞቼ እንዲመረጡልኝ ነው የምመኘው፡፡ ነገር ግን ይሄን ጥቆማ ላደረጉት ወገኖቼ በእግዚአብሔር ስም ምስጋናዬን አቀርባለሁ፡፡
ለእጩነት በመጠቆምዎ ምን ተሰማዎት? እንደሚመረጡ ጠብቀው ነበር?
እዚህ ደረጃ እደርሳለሁ፣ ጨርሶ እጠቆማለሁ የሚል ሀሳብ አልነበረኝም፡፡
በመጠቆሜም ደስተኛ አይደለሁም፡፡ ለምን ትለኝ እንደሆነ ከባድ ኃላፊነት ነው፡፡ ከአርባ ሚሊዮን በላይ የሆነውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶከስ ተዋህዶ ሕዝብ ማገልገል ከባድ ነው፡፡ እግዚአብሔር ከወደደ ደግሞ ይኼን ሕዝብ ለማገልገል አንተ እንደፈቀድክ ይሁን ብዬ ነው የተውኩት፡፡
ብዙ ቋንቋዎች እንደሚናገሩ ሰምቻለሁ----- ምን ያህል ይችላሉ?
አፌን የፈታሁት በኦሮምኛ ነው፡፡ አማርኛ፣ ግዕዝ፣ እንግሊዝኛ፣ ጀርመንኛና በመጠኑ ጣሊያንኛ እናገራለሁ፡፡ አማርኛን፣ ግእዝንና እንግሊዝኛን በትምህርት ቤት ነው የተማርኩት፡፡ ጀርመንኛን ቅድስት ቤተክርስትያን አሁን በህይወት ከሌሉት ከእነ ብፁዕ አቡነ ይስሀቅ ጋር ወደ ምዕራብ ጀርመን ልካኝ ነው የተማርኩት፡፡
በእነዚህ ቋንቋዎች በመግባባቴ ደስታ ይሰማኛል፡፡ ጣልያንኛውን ደግሞ ስድስት አመት ተኩል እዚያ በመቆየቴ ነው የቻልኩት፡፡ ኦሮምኛ በመናገሬ ደስታ ይሰማኛል፡፡ በኦሮሚያ ክልል ኦሮሚኛ ተናጋሪ ካህናት ጥቂት ናቸው፡፡
ከብሔረሰቡ ተመርጬ ጳጳስ በመሆኔ ይደንቀኛል፤ የእግዚአብሔር ምርጫ ነው፡፡ ተልእኮውን ያፋጥናል፡፡ ህብረተሰቡ በአስተዳደርም ሆነ በወንጌል ስብከት ይበልጥ በሚረዳው ቋንቋ ማስተማር እንዲሁም ከአካባቢው ህብረተሰብ ጋር ለመግባባት ቋንቋ መቻል ጥሩ ነው፡፡ ኦሮምኛ ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔር ከፈቀደ በርካታ ቋንቋዎችን ብችል እወዳለሁ፡፡ በቋንቋ አላመልክም፣ የማመልከው በኢትዮጵያዊነቴ ነው፡፡ በእምነቴ አማራ፣ ኦሮም በሚል አልከፋፍልም፡፡
ፓትርያርክ ቢሆኑ ለእርቀሰላሙ ምን ያህል ዝግጁ ነዎት?
ለእርቀሰላሙ እኔ ሳልሆን ቅዱስ ሲኖዶስ በወሰነው መሰረት መቀጠሉ ያስደስተኛል፡፡ ሊቃነጳጳሳቱ ሳይሆኑ ከጀርባቸው ያሉት ብሶት ያለባቸው ሁሉ ወደ እናት ሀገራችን ገብተው ሰላማዊ ኑሮ ቢኖሩ ደስተኛ ነኝ፡፡ ለእርቀሰላም ደግሞ ቅዱስ ሲኖዶስ በሩን ከፍቷል፡፡ በተከፈተው በር ገብተው ብፁአን ሊቃነ ጳጳሳት ሀገራቸውን እንደእኛ ቢያገለግሉ በጣም ደስተኛ ነኝ፡፡

=======================

ለፓትርያርክነት እጬ ሆነው መጠቆምዎን የሰሙት ከማነው?
ሲወራ ነው የሰማሁት፡፡ ከቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ በፊት ወሬ ይሰማል፤እውነትና ውሸትነቱ አይታወቅም እንጂ፡፡ በሲኖዶስ ጉባዔ በይፋ ተነገረኝ፡፡
የምረጡኝ ዘመቻ መሰል ነገር በሀገረስብከትዎ እንደነበር ሰምቻለሁ…
ኧረ እንዲህ አይነት እንቅስቃሴ መኖሩን አላውቅም፡፡ እንደውም ጐንደር ከአምስቶቻችን እጩዎች ውጪ የሆኑ ሊቀጳጳስ መርጠው ማስተላለፋቸውን ነው የማውቀው፡፡
ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ጋር ለፓትርያሪክነት ተወዳድረው ነበር፡፡ አሁን በእጩነት እንደሚመረጡ ጠብቀው ነበር?
አሁንም ሆነ ያን ጊዜ እጩ መሆኔን ተቃውሜ ነበር፡፡ ለቅዱስ ሲኖዶስም ይህንኑ ተናግሬአለሁ፡፡ የሲኖዶሱ አባላት ዝም ቢሉም አራታችን ተናግረናል፤ ሁላችንም ተናግረናል፡፡ ለማሟያ ነው ሊያሰኝም ይችላል፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ሲመረጡ የአስመራጭ ኮሜቴ ሊ/መንበር ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡ ብትተውኝ ግን ብዬ ማመልከቴ አልቀረም፡፡
ስድስተኛው ቅዱስ ፓትርያሪክ ቢሆኑ ቅድሚያ የሚሰጧቸው ተግባራት ምንድን ናቸው?
በዚያን ጊዜ ይገልፅልኝ ይሆናል፤አሁን ያሰብኩበት አይደለም፡፡
ለእርቀሰላሙ መቀጠል ትልቅ አስተዋፅኦ እንዳበረከቱ ይነገራል፡፡ እስቲ የሰሩትን ይንገሩኝ---
ከፍተኛ ጥረት ያደረግሁበት ነው፤አባታችን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስም እያሉ እኔ ሃያ አመት ደብረታቦር ተቀምጫለሁ፡፡ ሃያ አመት ሙሉ የፋርጣ እና የእስቴ የደቡብ ጐንደር ካህናት፤“አባታችን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያሪክ ሲሉ እንጂ አንድ ቀን እንኳ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ሲሉ አልተሰሙም፤እንዲህ ማለት ቅዱስነትዎን የቤተክርስትያንንም ስርዓት በመቀበል ነው እንጂ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስን ጠልተው አይደለም፡፡ አሁንም ይህ ሀገር ለቅዱስነትዎ ባለውለታዎ ነው፡፡ ስለዚህ ውለታዎን ለመክፈል ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ እንዲመጡ አሳስባለሁ” ብዬ ሁለት ሦስት ጊዜ ተናግሬአለሁ፡፡
መጥተው ሀገራቸው እንዲገቡ እንጂ በአቡነ ጳውሎስ ላይ ፓትርያሪክ እንዲሆኑ አይደለም፡፡ አቡነ መርቆሬዎስ አሁን መንበሩ ላይ እንዲቀመጡ የሚሉ አሉ፤ እንዲህ ያለ ሀሳብ የለኝም፡፡ ምኞታቸው ሀገራቸው መግባት ነውና ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ አሁን ሀገራቸው እንዲገቡ ነው እንጂ ፓትርያርክ እንዲሆኑ አይደለም፡፡
ይህ አቋሜ በአቡነ ጳውሎስም ጊዜ አሁንም ተመሳሳይ ነው፡፡ ሰላሙ እንዳይንጠለጠል ነበር ምኞቴ፡፡ ሰላሙ እየተወለካከፈ እዚህም እዚያም ያሉት እያስቸገሩ ስለሆነ በተረጋጋ ጊዜ ይሻላል፤ አሁን ቤተክርስትያኒቱን የሚመራ አባት ይመረጥ ብለናል፡፡
ብፁዕነትዎ ፓትርያሪክ ቢሆኑ እርቀሰላሙ ከምን ይደርሳል? በምን ያህል ጊዜስ ይጠናቀቃል?
የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው እንጂ ትንቢት አልተናገርንም፡፡ ፓትርያሪክም ብሆን ሊቀጳጳስም ብሆን እርቁ ይቀጥላል፡፡ እዚህም ያሉት እዚያም ያሉት ቤተክርስትያን እንድትከፈል አይፈልጉም፡፡ ቤተክርስትያን እንዳትከፈል እርቁም እንዲጠናቀቅ ነው ምኞቴ፡፡
በስደት ካሉ ብፁአን አባቶች ጋር ጥብቅ ግንኙነት አለዎት ይባላል፤እውነት ነው?
በስደት ካሉት ብፁአን አባቶች ጋር ተገናኝተንም አናውቀም፡፡ ሆኖም ስዊድን ያሉት አቡነ ኤልያስ ደብረታቦር ሳለሁ ይደውሉልኝ ነበር፡፡
ብዙ ጊዜ በቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ አይገኙም ---- ለምንድነው?
ብዙ ጊዜ አልመጣም፡፡ ሀገሩም ሩቅ ስራውም ከባድ ነው፡፡ በዚያ ላይ ስራው ይበዛል፡፡ ደብረታቦርም ሳለሁ በዓመት አንድ ጊዜ ነው የምመጣው፡፡ ይህ በሌላ ምክንያት ወይም ከፓትርያሪኩ ክፍተት ኖሮን አይደለም፡፡ አቡነ ጳውሎስ እንደውም ወዳጄ ናቸው
አቡነ ጳውሎስ ሰሩት ከሚባሉ በጎ ሥራዎች የሚያደንቁት አለ?
ብዙ በጐ ተግባራት ነበሯቸው፡፡ ይህን የጳጳሳት መኖርያና መንበረ ፓትርያርክ አሰርተዋል፡፡ እንግዳ ተቀባይም ነበሩ፡፡ የመጣውን እንግዳ ማብላት ማጠጣት ይወዳሉ፡፡ ቤተክርስትያን ማገልገል ይወዳሉ፡፡አቡነ ጳውሎስን “ይኼ ስህተት ነው” ብለው የተናገሩበት ጊዜ አለ?
ሰው አብሮ ከኖረ እንዲህ ቢሆን ይሻላል መባባል አይቀርም፡፡ ለምሳሌ ደብረታቦር አይሄዱም ነበር በስደተኞቹ ይሁን በሌላ ከበድ ይላቸው ነበር፡፡ ብዙዎቹ ውጭ ያሉት ብፁአን አባቶች ከዚያ አካባቢ ናቸው፡፡
አንድ ጊዜ ስለ ኤችአይቪ ለማስተማር፤ቡራኬም ለመስጠት፤ የሠራናቸውን ትምህርት ቤትና ቤተክርስትያን እንዲባርኩልን በሃያ አመቱ ውስጥ አንዴ ለመሄድ ፈቃዳቸው ሆኖ ነበር፡፡
እናም “ደብረታቦር ልንመጣ ነው፤ ጐብኝተን ምዕዳን ሰጥተን እንመለሳለን፤ አናድርም ባህርዳር ነው የምናድረው” አሉኝ፡፡ “ለአንድ ቀን መጥቶ የሚመለስ ሰው ወይ ለለቅሶ ወይ ዘመድ ለመጠየቅ ይመስላል እንጂ የፓትርያርክ ጉብኝት አይመስልም----” ብዬ ተከራክሬአቸው፤ የአውሮፕላን ትኬት አስቀይረው አርብ ሄደው እስከ እሁድ ቆይተዋል፡፡

በስደት ላይ የሚገኘው ሲኖዶስ ሢመት ፕትርክናውን አውግዟል
‹‹ዕርቀ ሰላሙ ቅዱስ ሲኖዶስ በተናገረው መሠረት ይቀጥላል››
/ተመራጩ ፓትርያርክ/
አምስት ዕጩ ፓትርያርኮች ለውድድር በቀረቡበት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የስድስተኛው ፓትርያርክ ምርጫ÷ ብፁዕ አቡነ ማትያስ 500 ድምፅ በማግኘት ሌሎች ዕጩዎችን በሰፊ ልዩነት ያሸነፉበት ውጤት የምርጫውን ተሳታፊዎችና ተከታታዮች እያነጋገረ ነው፡፡
አዲስ አድማስ ያነጋገራቸው የምርጫው ተሳታፊዎችና በተለያዩ መንገዶች የምርጫውን ሂደት የተከታተሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልጋዮችና ምእመናን÷ የምርጫው አሸናፊ ብፁዕ አቡነ ማትያስ ሊኾኑ እንደሚችሉ ከወራት በፊት በሰፊው ሲነገር የቆየ ነበር፡፡ ይኹንና በምርጫው ድምፅ ከሰጡ 806 መራጮች መካከል ከ60 በመቶ በላይ ድምፅ በማግኘት ያሸነፉበት ውጤት÷ በዕጩነት ከተካተቱትና ለፓትርያርክነት ይበቃሉ የተባሉት ሌሎች ዕጩ ፓትርያሪኮች በተናጠል ካገኟቸው አነስተኛ ድምፆች አንጻር የምርጫውን ሂደት መለስ ብለው ለማጤን እንዳስገደዳቸው ይገልጻሉ፡፡
ስማቸውና የተወከሉበት አህጉረ ስብከት እንዳይገለጽ የጠየቁ ሁለት መራጮች፣ ከትላንት በስቲያ በመንበረ ፓትርያሪክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ የተከናወነውን የስድስተኛው ፓትርያርክ ምርጫ ከጅምሩ እስከ ፍጻሜው በቅርበት መከታተላቸውን፣ በአፈጻጸሙ ግልጽና ቀልጣፋ ከመኾኑም ባሻገር ለትችት የሚዳርግ የጎላ ችግር እንዳላዩበት አስረድተዋል፡፡ ይኹንና ከምርጫው ቀን በፊትና ምርጫው ከተካሄደበት አዳራሽ ውጭ ተፈጽመዋል የሚሏቸው ተግባራት ለተጠቀሰው የውጤት መራራቅ በምክንያትነት አስቀምጠዋል፡፡
አስተያየት ሰጭዎቹ በቅድመ ምርጫው ተፈጽመዋል ከሚሏቸው ተግባራት መካከል÷ መንግሥት አሸናፊው ዕጩ ብፁዕ አቡነ ማትያስ ‹‹ቀጣዩ ፓትርያርክ እንዲኾኑ ይደግፋል›› በሚል በሰፊው መወራቱና ይህንንም ተከትሎ በመራጮች ውሳኔ ላይ ተጽዕኖ ለማሳደር ተፈጽሟል የሚሉት መጠነ ሰፊ ቅስቀሳ ነው፡፡ ቅስቀሳው በተወሰነ መልኩ ‹‹ብፁዕነታቸውን ባትመርጡ…›› የሚል ማስፈራሪያም የተቀላቀለበት እንደነበር መራጮቹ የራሳቸውንና የሌሎች ጓደኞቻቸውን ተሞክሮ በመጥቀስ ይናገራሉ፡፡
በርካታ የካህናትና ምእመናን ጥቆማ ካገኙና በዕጩ ፓትርያሪክነት ለመወዳደር ይበቃሉ ያሏቸው ሊቃነ ጳጳሳት በዕጩነት አለመካተታቸው ቅር እንዳሰኛቸው የገለጹት እኒህ አስተያየት ሰጭዎች÷ በምርጫው ለቀረቡት ዕጩዎች በአስመራጭ ኮሚቴው የተሰጠው ትኩረትም ምክንያታዊና ሚዛናዊ አለመኾኑንም ለውጤቱ መራራቅ በመንሥኤነት ጠቅሰዋል፡፡ በድምፅ መስጫው ወረቀት ላይ አሸናፊው ዕጩ ብፁዕ ማትያስ በመጀመሪያ ደረጃ መቀመጣቸው በሢመተ ጵጵስና ዘመነኛቸው ከኾኑት፣ በዕድሜ ከሚበልጧቸውና በሁለተኛ ደረጃ ከተቀመጡት ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ አንጻር የራሱ ተጽዕኖ አሳርፏል ብለው እንደሚያምኑ ገልጸዋል፡፡
የሁለቱን አስተያየት ሰጭዎች አስተያየት የሚተቹትና ድምፃቸውን ለአሸናፊው ዕጩ መስጠታቸውን ገልጠው የተናገሩ ሌሎች መራጮች በበኩላቸው÷ ብፁዕ አቡነ ማትያስ በአባታዊ ሞገሳቸው፣ በአገልግሎት ልምዳቸውና በዓለም አቀፍ ተሞክሯቸው ያገኙት ድምፅ ውጤት የሚያንሳቸው እንጂ የሚበዛባቸው እንዳልኾነ ይከራከራሉ፡፡ በቅድመ ምርጫው በየአቅጣጫው በብፁዕነታቸው ላይ ሲሰጡ የቆዩ ትችቶችን መከታተላቸውን የገለጹት መራጮቹ÷ በመጨረሻ ለውጤቱ ወሳኝ የሚኾነው መራጩ የሚወስደው አቋም ነውና በዕጩነት ከቀረቡት ሊቃነ ጳጳሳት ብፁዕነታቸው በሰፊ ድምፅ መርተው የተመረጡበት ውጤት ተቺዎቻቸውን ጭምር ያስደነቀ መኾኑን በምርጫው ስፍራ ማረጋገጣቸውን መስክረዋል፡፡
በምርጫው በዕጩ ፓትርያሪክነት የተወዳደሩት ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ 98 ድምፅ፣ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ 98 ድምፅ፣ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል 70 ድምፅ እና ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ 39 ድምፅ ማግኘታቸው አስመራጭ ኮሚቴው ይፋ ባደረገው የምርጫ ውጤት ተገልጧል፡፡
ከምርጫው አንድ ቀን በፊት ከአዲስ አድማስ ዘጋቢ ጋር አጭር ቆይታ ያደረጉት ተመራጩ ፓትርያሪክ ብፁዕ አቡነ ማትያስ በዕጩነት መካተታቸውን ያወቁት በሀ/ስብከታቸው ኢየሩሳሌም ሳሉ ከኢትዮጵያ በተደረገላቸው ጥሪ መኾኑን ገልፀዋል፡፡ “መንግሥት እርሳቸው ስድስተኛው ፓትርያሪክ እንዲኾኑ ይፈልጋል ስለመባሉ ተጠይቀው÷ ‹‹ስለዚህ ጉዳይ ምንም የማውቀው ነገር የለም፤›› ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
በሌላ በኩል በሰሜን አሜሪካ በስደት ላይ የሚገኘው ‹‹ሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ›› የካቲት 24 ቀን 2005 ዓ.ም የሚካሄደው ሢመተ ፓትርያሪክ÷ ‹‹ኢ-ቀኖናዊና የቤተ ክርስቲያንን ክብር ዝቅ የሚያደርግ፣ ሥርዐተ አልበኝነትን የሚሰብክ፣ ቤተ ክርስቲያንን የሚከፋፍል ነው፤›› በሚል ቀደም ሲል ያስተላለፈውን ውግዘት ማጽናቱን ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡ በመላው ዓለም የሚገኙ ካህናትና ምእመናን ለቤተ ክርስቲያን ክብርና አንድነት፣ ሰላምና ሐዋርያዊ ተልእኮ መሳካት አብረውት እንዲቆሙና እንዲሠሩም ጥሪውን አስተላልፏል፡፡
በውጭ በስደት ከሚገኙት የቤተ ክርስቲያኒቱ አባቶች ጋር የተጀመረውን የዕርቀ ሰላም ንግግር ለፍጻሜ ከማብቃት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን ተቋማዊ መሻሻል በማፋጠን አስተዳደራዊ ለውጥ እንዲመጣ ከመንቀሳቀስ አኳያ በርካታ ተግባራት የሚጠብቋቸው አሸናፊው ተመራጭ ፓትርያሪክ ብፁዕ አቡነ ማትያስ ለአዲስ አድማስ እንደገለጹት÷ ‹‹ቤተ ክርስቲያኒቱ ቀጥተኛውንና ትክክለኛውን መንገድ እንድትይዝና መንፈሳዊነትን እንድትጎናጸፍ ነው ተስፋ የማደርገው፡፡ ዕርቀ ሰላሙ እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ተናግሯል፡፡ በዚያው መሠረት ይቀጥላል፡፡ ከሲኖዶስ የተለየ ሐሳብ ሊኖረኝ አይችልም፤›› ብለዋል፡፡
በአስመራጭ ኮሚቴው በወጣው መርሐ ግብር መሠረት የስድስተኛው ፓትርያሪክ በዓለ ሢመት በነገው ዕለት የአኀት አብያተ ክርስቲያን ተወካዮችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንደሚፈጸም መገለጹ ይታወሳል፡፡