Administrator

Administrator

Saturday, 23 March 2024 20:51

ናፍቆቴ ዳርቻው

ዥው ብዬ
ወደ ታች እምዘገዘጋለሁ
በሀይል
ቁልቁል እወርዳለሁ
እናም ትንፋሽ አጥሮኝ
መሬት ርቆኝ
አለቅሁ ተሳቅቄ
ኧረ ናፍቆኛል መውደቄ፡፡
****




Saturday, 23 March 2024 20:49

ዱር ሃገሬ

ልቤን ጫካ አደረግሁት
ልቤን ዱር አደረግሁት
ይኸው ዛሬ
ስጎበኘው ተዟዙሬ
ሰፍሮበታል የአገር አውሬ፡፡
(ዳዊት ጸጋዬ፤ 2016)

አንድ የጣሊያን አፈ-ታሪክ እንዲህ ይላል።
አንድ የታወቀ ክራክ የሚባል ሌባ ነበር ይባላል። ይህንን ሌባ ማንም ሊይዘው አልቻለም። ይህ ክራክ የተባለው ሌባ ደግሞ ክሩክ የሚባለውን ሌላ ሌባ ለማግኘት ከፍተኛ ምኞት ነበረው።
አንድ ቀን ክራክ ምሳውን ሊበላ አንድ ሆቴል ገብቶ፣ ከአንድ ሌላ ተመጋቢ ራቅ ብሎ ይቀመጣል። ሰዓት ለማየት ወደ እጁ  ሲመለከት ሰዓቱ ተሰርቆበታል።
“እኔ ሳላውቅ ሰዓቴን ከእጄ ላይ አውልቆ ሊወስድ የሚችል ክሩክ መሆን አለበት” አለ በሆዱ።
በዚህ ቁጭት ብድግ ይልና ግራና ቀኝ ዘወር ዘወር ብሎ ምግብ እየበላ ወዳለው ሰው ተጠግቶ በከባድ ቅልጥፍና የሰውዬውን ቦርሳ ይመነትፈዋል።
እንግዳው ተመጋቢ ሂሳብ ሊከፍል ኪሱ ሲገባ ቦርሳው የለም። ያለምንም ማመንታት ወደ ክራክ ዘወር ብሎ፤
“አንተ ክራክ መሆን አለብህ” አለ።
“ትክክል ነህ” መለሰለት።
“እንግዲያው አብረን እንስራ?” አለው።
“መልካም” አለ ክሩክ።
ጊዜ ሳይፈጅባቸው ተስማሙና አብረው ወደ ከተማ አመሩ። ከዚያም ወደ ንጉሡ ሀብት ማከማቻ ካዝና ሄዱ። ካዝናው በበርካታ ዘቦች ተከቧል። ያም ሆኖ ሌቦቹ ምድር ለምድር መግቢያ ጎርጉረው ገቡ። ያለውን ሀብት ሁሉ ሰርቀው ወጡ።
ንጉሡ የሚያደርጉት ግራ ገባቸው። ሌቦቹ እነማን እንደሆኑ ለማወቅ ችግሯቸው ሰነበቱና ቀጥታ ወደ እስር ቤት አመሩ። አንድ በሌብነት የታሰረ ሰው ጋር ሄዱና፤
“ማን እንደሰረቀኝ ከነገርከኝ በነፃ እንድትለቀቅ አደርጋለሁ” አሉት።
እስረኛውም፤ “ያለጥርጥር  ወይ ክራክ ወይም ክሩክ ወይም ሁለቱም መሆን አለባቸው። እንዴት ሊይዟቸው እንደሚችሉ እነግርዎታለሁ። የስጋ ዋጋ ከዛሬ ጀምሮ በኪሎ 100 ብር ገብቷል ይበሉና ያውጁ። ያንን ከፍሎ የሚገዛ ያ የእርስዎ ሌባ ነው።”
ንጉሡ የሥጋ ዋጋ 100 ብር አስገቡ። ሥጋ የሚገዛ ሰው ጠፋ። ሲረፋፍድ ግን አንድ ቄስ እንደገዛ ወሬው ተሰማ።
ይሄኔ እስረኛው፤ ”በቃ ወይ ክራክ ወይ ክሩክ በቄስ ተመስለው ሥጋ ገዙ ማለት ነው። አሁን እኔ እንዳልታወቅ ተሸፋፍኜ በየቤቱ እየዞርኩ እለምናለሁ። ሥጋ የሚሰጠኝ ሰው ካገኘሁ በሩ ላይ ቀይ ምልክት አደርጋለሁ። የእርስዎ ዘቦች እንግዲህ ተከትለው ሌቦቹን ማሰር ነው” አለ።
እስረኛው በዘዴ ተጠቀመ። እንዳለው በክራክ ቤት ላይ ቀይ ቀለም ምልክት አደረገ። ዳሩ ምን ያደርጋል፤ ሌባው ክራክ ምልክቱን አየውና በከተማው ባሉ ቤቶች በሮች ላይ ሁሉ ቀይ ምልክት አደረገባቸው። በመካያው የክራክና የክሩክ መኖሪያ ቤት የት እንደሆነ ሳይታወቅ ቀረ።
እስረኛው አሁንም ሌላ ዘዴ ዘየደ። “እነዚህ ሌቦች መቸገራቸው አይቀርም። ስለዚህ እንደገና የእርስዎን ሀብት ሊሰርቁ መምጣታቸው አይቀርም። ከደረጃው ግርጌ የሚፈላ ውሃ ያስቀምጡ። ሌቦቹ በጨለማ ወደ ምድር ቤት እንወርዳለን ሲሉ ውሃ ውስጥ ይገባሉ” አላቸው።
ንጉሡ እንደተባለው አደረጉ።
ሌቦቹ እውነትም ሲቸግራቸው ወደ ንጉሡ ካዝና መጡ። ክሩክ ቀድሞ ገባ። ጨለማ ስለነበረ በቀጥታ የፈላ ውሃ ካለበት በርሜል ውስጥ ጥልቅ አለ። ጓደኛው ሊያወጣው ሲሞክር አልተሳካለትም። ስለዚህ የክሩክን አንገት ቆርጦ እዛው ሬሳውን ጥሎት ሄደ።
ንጉሡ በነጋታው ሄደው ሌባው መያዙን አዩ። ግን ጭንቅላቱ ተቆርጦ ስለተወሰደ ማንነቱ የማይለይ ሆነ። አሁንም እስረኛው ሌላ ዘዴ ነገራቸው። “ሬሳውን በከተማ መሃል በፈረሶች ያስጎትቱት። ሬሳውን አይቶ የሚያለቅስ ሰው ከሰሙ የሌባው ቤት እዛ ነው ማለት ነው።”
እውነትም የክሩክ ሚስት ሬሳውን ስታይ ጮኸች። ሆኖም ይሄ አደገኛ መሆኑን የተገነዘበው ክራክ፤ ሰሀንና የቤት እቃ እየወረወረ  ሴትየዋን እየደበደበ ቆየ። ዘቦቹ ድምጽ ወደሰሙበት ቤት ገቡ። ያገኙት ግን ሚስቱ የቤት እቃ በመስበሯ ምክንያት የሚደበድብ ባል ብቻ ነው።
በመጨረሻ፤ ንጉሡ ሲጨንቃቸው፤ ሀብቴን የዘረፈውን ሌባ እምረዋለሁ። ግን አንድ ነገር ማድረግ ከቻለ ነው። ይኸውም የምተኛበትን አንሶላ ከሰረቀ ነው። ክራክ ፊት ለፊት መጥቶ ”እኔ እችላለሁ፤” አለ።
ያን ማታ ንጉሡ ሽጉጣቸውን ይዘው አልጋቸው ውስጥ ገቡ። ክራክ ከመቃብር ቆፋሪዎች ዘንድ ሬሳ ይዞ መጣ። የራሱን ልብስ አልብሶ ቤተ-መንግስቱ ጣራ ላይ አንጠለጠለው። እኩለ-ሌሊት ከጣራው ወደ ንጉሡ መኝታ ቤት መስኮት ሬሳውን ላከው። ንጉሡ ክራክ ነው ብለው ሬሳውን ደበደቡት። መሬት ወደቀ። ተነስተው ከፎቅ ወርደው የወደቀውን የክራክ ሬሳ ሊያዩ ሄዱ። ይሄኔ ክራክ በመስኮቱ ገብቶ የንጉሡን አንሶላ ጠቅልሎ ውልቅ አለ።
ንጉሡ ምህረት አደረጉለት። ልጃቸውንም ዳሩለት። ክራክም ሁለተኛ ላይሰርቅ ቃል ገባ!
***
ሌቦች በችሎታ የሚፎካከሩባት ሀገር ያልታደለች ናት። ሌባ ለመፈለግ ሌባ ማማከር እርግማን ነው። ሌባውን ካገኘህልኝ በነጻ እለቅሃለሁ ማለት ደግሞ የከፋ እርግማን ነው። በየበሩ ላይ ቀይ ምልክት ከሚያደርግ ሌባ ይሰውረን። ጭንቅላቱ ተቆርጦ ማንነቱ የማይለይ  ሌባ አይጣልብን፡፡ የምንተኛበትን አንሶላ ጭምር ለሚሰርቅ ሌባ እድል የሚሰጥ አዋጅ፤ መመሪያ፣ ፖሊሲ አያምጣብን። ሌቦቻችንን መያዝ ከባድ ነው። ታክቲክ እየለዋወጡ ሌብነት የሚያጧጡፉ ሌቦችን በቁጥጥር ስር ማዋል ትልቅ ተግባር ነው። ሌብነትና አያሌ መልኮቹ የጥቅል ስማቸው ሙስና ነው። ዛሬም እንደ ትላንት እግር እስኪነቃ ሲሄዱ ቢውሉ በዚህም ሆነ በዚያ ዘዴ በሀገራችን ይህ አባዜ ያልተጠናወተው መ/ቤትና ተቋም አይገኝም፤ ብንል ከሀቁ አንርቅም። በተናጽሮ ሲታይ ጥንት “ደሞዙን 250፣ የሚኖረው ቪላ ቤት፣ የሚነዳው ውድ ውድ መኪና!” በሚል ምጸታዊ መፈክር ሙስናን ለመዋጋት፤ ይሳካም አይሳካም መሞከሩ አይዘነጋም። ዛሬም መሰል መፈክር ማስገር የሚያስፈልግበት ደረጃ የደረስን ይመስላል። ጥንትም የነበረው ችግር ዛሬም እንዴት ሊኖር ቻለ? “በሥራው አጋጣሚ በእጁ የገባውን የመንግስትና የህዝብ ገንዘብ የዘረፈው” የሚለው አባባል ትላንት ነበር፤ ዛሬም አለ። ነገሩ እንግሊዞች “Who judges the judges?” “ዳኞቹን ማን ይዳኛቸው?” የሚለው ቁልፍ ጥያቄ ዙሪያ ያጠነጠነ ነው። ተቆጣጣሪውን ማን ይቆጣጠረው? ገምጋሚውን ማን ይገምግመው? እንደማለት ነው። ሌላው መነሳት ያለበት አባባል፤ They shout at most against the vices they themselves are guilty of የሚለው ነው፡፡ በአማርኛ ሲታሰብ፤  “ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮሃል” የሚል የሼክስፒር አባባል መሆኑ ነው።
ዛሬ አዲስ የሚሾሙ ባለስልጣኖች ስለማናቸውም ጉዳዮች ሲጠየቁ፤ “ከጥንት የወረስነው አሰራር”፣ “ያለፈው ስርዓት የጣለብን እዳ”፣ “ባለፈው ጊዜ የነበረው አሰራር ዝርክርክነት” ወዘተ የሚል ነው፤ የመልሳቸው መነሻ ሃረግ። ከቶውንም እንደ ሰንሰለት ተሳስሮ ባለው የቢሮክራሲ አውታር፣ ሰው የሰውን ኪስ እንደራሱ በሚያውቅበት የእከክልኝ ልከክልህ አገር፣ ከጎኑ አንድ ባለስልጣን ሲነሳ ወዲያውኑ “ያለፈው አሰራር፣ ያለፈው ስርዓት” የሚባለው እንዴት ነው? ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል የሚባለውን የቁርጥ ቀን ተረት አንርሳ እንጅ!
ሹም ሽረት በተደረገ ቁጥር አሮጌውን መኮነንና አዲሱን ጻድቅ ማድረግ የተለመደው የአገራችን ፈሊጥ ነው። ከዚህ መጠንቀቅ አለብን። ከዜሮ የሚጀምር ልማት የለም። መልካም ፍሬ ያላፈሩ፣ ውጤት ያላስመዘገቡ፣ ድርብ ስራ የሚሰሩና የተዘጉ፣ ብቃትና ስኬት የሌላቸው ወዘተ… የሚሉ ግምገማዎች ስንል ፈጠው የወጡትን ጉድለቶች አብሮ መመርመርና በአግባቡ መገምገም  ይኖርባቸዋል። ማመን ብቻ ሳይሆን መተማመን ያስፈልጋል። አሁንም ሙያ፤ ስነ-ምግባርና ልምድ ወሳኝ መሆን አለባቸው።
ዝውውሮች በተፈተሸ አቅም የተጤኑ፣ ከአንዱ ኃላፊነት ገለል ብሎ ይሂድ ብቻ የማይባልባቸው መሆን አለባቸው። የሁሉ መ/ቤቶችና ተቋማት ጤና የአገሪቱ አጠቃላይ ጤና ነው። የሰራ-አከላቷ በትክክል መንቀሳቀስ ነው ለደህንነቷ ዋስትና የሚሆነው። አለበለዚያ ቴዎድሮስ እንዳለው፤
“መች ትተርፊያለሽ ኢትዮጵያ፤ ህዋስሽ አብሮኝ ካልሰራ
አንገትሽ ብቻ መቅደላ፣ አፋፍ ወጥታ ብትበራ…”
(የቴዎድሮስ ስንብት ከመቅደላ)
ማለት እንዳይሆን የመጨረሻ ቃላችን፤ መጠንቀቅ ተገቢ ነው። “ላም ባንድ ጎኗ አትሰባ፤ ባንድ ጎኗ ጉፋያ አትሆን” ይሏል ይሄው ነው።

  የማይመልሱ ሰዎችን ፎቶና ማንነት በሚዲያ ይፋ አደርጋለሁ ብሏል
         - የራስ ያልሆነ ገንዘብ ህጋዊ ማድረግ እስከ 25 ዓመት እስራት ያስቀጣል
         - የአካውንቶች መታገድ ገንዘቡን ለመመለስ እንቅፋት ፈጥሯል ተብሏል


          የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አጋጠመኝ ባለው  የሲስተም ችግር ምክንያት ያለአግባብ  ገንዘብ ከባንኩ  የወሰዱ ወይም ወደ አካውንቶች  ያስተላለፉ ግለሰቦች የወሠዱትን ገንዘብ ለባንኩ እንዲመልሱ የሠጠው የጊዜ ገደብ ዛሬ ያበቃል።  በተሰጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ ገንዘቡን  ካልመለሱ ፎቷቸውንና ማንነታቸውን በመገናኛ ብዙኃን ይፋ እንደሚያደርግም ገልጿል ።
ባንኩ መጋቢት 6 ቀን 2016 ዓ.ም በተፈጠረው የሲስተም ችግር ምክንያት ከባንኩ  ገንዘብ የወሰዱ ወይም ወደተለያዩ ሂሳቦች ያስተላለፉ ግለሰቦች ገንዘቡን ተመላሽ እንዲያደርጉ ተደጋጋሚ ጥሪ ያቀረበ መሆኑን አመልክቶ፤  የመጨረሻ  ያለውን ጥሪ ከትላንት በስቲያ  ሐሙስ መጋቢት 12 ቀን 2016 ዓ.ም.  አስተላልፏል። በዚህ ጥሪ መሠረትም ባንኩ ገንዘቡን ለማስመለስ የሠጠው የጊዜ ገደብ ዛሬ ይጠናቀቃል ።
ገንዘቡን ተመላሽ በማያደርጉ ሰዎች ላይ በሕጋዊ ሂደቱ ተገቢ ውሳኔ እስኪገኝ ድረስ ፎቶግራፋቸውንና ዝርዝር ማንነታቸውን የሚገልጹ መረጃዎች፤ ባንኩ በመረጠው የብዙኃን መገናኛ መንገድ ለሕዝብ ይፋ እንደሚያደርግም አስታውቋል። ከሕግ አካላት ጋር በመተባበር የግለሰቦችን ስም ዝርዝር በየቅርንጫፎችና እንደሁኔታው ግለሰቦቹ ሊታወቁ በሚችሉበት አካባቢ ይፋ በማድረግ ቀጣይ ሕጋዊ እርምጃዎችን እንደሚከተሉም  ገልጿል። በተጨማሪም “ከፍትህ አካላትና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በመተባበር ተገቢውን የወንጀል፣ የፍትሐ ብሔር እንዲሁም አስተዳደራዊ እርምጃዎች እንዲወሰዱ እንደሚያደርግም አሳስቧል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ ከንግድ ባንክ የራሳቸው ያልሆነ ገንዘብ ያንቀሳቀሱ ግለሰቦች የማይመልሱ ከሆነ፣ በህግ እንደሚጠየቁ የፋይናንስ ደህንነት አገልግሎት ከትላንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡ በተፈጠረው ችግር ዙሪያ ከባንኩ ጋር በጋራ እየሰራ እንደሚገኝ የገለፀው የፋይናንስ ደህንነት አገልግሎቱ፤ የራስ ያልሆነን ገንዘብ ህጋዊ ማድረግ እንደ ወንጀሉ ክብደት እስከ 25 ዓመት በሚደርስ እስራት እደሚያስቀጣ አሳስቧል፡፡
ባንኩ አርብ መጋቢት 6 ቀን 2016 ዓ.ም. ምሽት ላይ የሲስተም ችግር በገጠመው ወቅት የተወሰደበት ገንዘብ  መጠን ከባንኩ በይፋ ባይገለጽም ፣ በዕለቱ የተወሰደው የገንዘብ መጠን 2.4 ቢሊዮን ብር (40 ሚሊዮን ዶላር) መሆኑን አሶሺየትድ ፕሬስ  ዘግቧል።

  -  ባለፈው ዓመት 7 ሺህ የሚጠጉ የሳይበር ጥቃት ሙከራዎች ተደርገዋል
ኢትዮጵያ ለሳይበር ጥቃት ተጋላጭነታቸው ከፍ ካሉ ሀገራት  መካከል አንዷ እንደሆነችና የሳይበር ጥቃቶቹ  የፋይናንስና የፀጥታ ተቋማትን፣ ባንኮችን፣ እንደ ቴሌኮምና መብራት ሃይል ያሉ  ተቋማትን፣ መሰረተ ልማቶችንና  ቁልፍ የመንግስት ተቋማትን  ኢላማ ያደረጉ እንደሆኑ  ታዋቂው የሳይበር ደህንነት ተቋም ሲዮን ገልጿል።
ተቋሙ ከትናንት በስቲያ  ይፋ ያደረገው መረጃ እንደሚያመለክተው፤  ዓለማችን በኢንተርኔት መተሳሰሯና በዲጂታል ቴክኖሎጂ ጥገኝነቷ በፍጥነት እያደገ መሄዱን ተከትሎ የሳይበር ጥቃትም ፈተና ሆኖባታል። ባለፈው የፈረንጆቹ አመት ከ340 ሚሊየን በላይ ሰዎችን ተጎጂ ያደረጉ የሳይበር ጥቃቶች ተፈጽመዋል ።
ግለሰቦችን፣ ተቋማትን እና የመንግስት መስሪያ ቤቶችን ኢላማ ባደረጉ የሳይበር ጥቃቶች፣ በ2023 ብቻ ከ8 ትሪሊየን ዶላር በላይ የሚገመት ጉዳት ደርሷል።
የሳይበር ጥቃት የትኛውንም ሀገር ወይም ተቋም ለይቶ እንደማይተው የሚገልጸው ታዋቂው የሳይበር ደህንነት ተቋም ሲዮን፥ ጠንካራ የሳይበር ደህንነት ህግና ቴክኖሎጂ ያላቸው ሀገራት አደጋውን መቀነስ መቻላቸውን ገልጿል።
በአንጻሩ ደካማ የሳይበር ደህንነት ህግ ያላቸው አልያም ከነጭራሹ የሌላቸውና ጥቃቶችን አስቀድሞ ለመመከት የሚጠቀሟቸው ቴክኖሎጂዎች ከፈጣኑ የዲጂታል አለም ጋር አብሮ በማይሄድባቸው ሀገራት አደጋው እንደሚከፋም ጠቁሟል።
በዚህም መሰረት ለሳይበር ጥቃት ተጋላጭነታቸው ከፍ ያሉ ናቸው በሚል  በተቋሙ  ከተጠቀሱ ሀገራት መካከል  ኢትዮጵያ የምትገኝ ሲሆን፤ አገሪቱ  ለሳይበር ጥቃት ተጋላጭ በመሆን ከአለማችን  በ8ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች  ብሏል።
ባለፉት ጥቂት አመታት በኢትዮጵያ የሳይበር ምህዳሩን የሚጠቀሙ ሰዎች ቁጥር መጨመርን ተከትሎ፣ በግለሰቦችና ተቋማት ላይ የሚሰነዘሩ የሳይበር ጥቃቶችን ጨምሮ በሀገሪቱ  ቁልፍ የመንግስት መሰረተ-ልማቶች ላይ እየደረሱ ያሉ ጥቃቶች የብሄራዊ ደህንነት ስጋት መሆናቸውን የኢንሳ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ሶካ  የሚታወስ ሲሆን፤  ባሳለፍነው ዓመት 2015 ዓ.ም  ከ 6 ሺ 959 በላይ  የሳይበር ጥቶች መፈጸማቸውንም ጠቁመዋል።
ከሳይበር ጥቃቶቹ ውስጥም 2 ሺ 559 ያህሉ በድረ ገጽ ላይ የተፈጸሙ ሲሆኑ፤ 1 ሺህ 295 ያህሉ ደግሞ የማልዌርና የፒሺግ መሆናቸው ተጠቁሟል። እንዲሁም 603 በመሰረተ ልማት ቅኝት፣ 1 ሺህ 493 መሰረት ልማት የማቋረጥ (አብዛኛው የፋይናንስ ተቋማትን ኢላማ ያደረገ)፣ 695 ሰርጎ የመግባት ሙከራ እና 145 ሌሎች የሳይበር ጥቃት ሙከራዎች ተደርገዋል።
የሳይበር ጥቃቶቹ የፋይናንስና የፀጥታ ተቋማትን፣ እንደ ቴሌኮምና መብራት ያሉ ቁልፍ ተቋማት መሰረተ ልማቶችንና  ቁልፍ የመንግስት ተቋማትን  ኢላማ ያደረጉ ነበሩ ተብሏል። በ2015 የተሰነዘሩ የሳይበር ጥቃት ሙከራዎችን መከላከል በመቻሉም፣ በሀገር ላይ ሊደርስ የነበረ 23.2 ቢሊየን ብር ኪሳራ ማዳን መቻሉን የኢንሳ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ሶካ ማስታወቃቸው አይዘነጋም ።

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ባጋጠመው የሲስተም ችግር ወቅት ገንዘብ የወሰዱ ወይም ያስተላለፉ ግለሰቦች እስከ መጪው ቅዳሜ መጋቢት 14 ቀን 2016 ዓ.ም. ድረስ ካልመለሱ ፎቷቸውንና ማንነታቸውን በመገናኛ ብዙኃን ይፋ እንደሚያደርግ አስታወቀ።

ባንኩ ገንዘቡን ተመላሽ በማያደርጉ ሰዎች ላይ በሕጋዊ ሂደቱ ተገቢ ውሳኔ እስኪገኝ ድረስ ፎቶግራፋቸውንና ዝርዝር ማንነታቸውን የሚገልጹ መረጃዎች “ባንኩ በመረጠው የብዙኃን መገናኛ መንገድ ለሕዝብ ይፋ አደርጋለሁ” ሲል አሳስቧል።

ገንዘብ የወሰዱ ወይም ወደተለያዩ ሂሳቦች ያስተላለፉ ግለሰቦች በአቅራቢያቸው ወደሚገኙ የባንኩ ቅርንጫፎች በመቅረብ እንዲመልሱም የመጨረሻ ጥሪውንው ዛሬ ሐሙስ መጋቢት 12 ቀን 2016 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አስተላልፏል።

ነገር ግን ይህ ሳይሆን ገንዘቡን በተቀመጠው ጊዜ ገደብ ተመላሽ የማያደርጉ ግለሰቦች ላይ የተለያዩ እርምጃዎችን እወስዳለሁ ሲል አስጠንቅቋል።

የሚወስዳቸው እርምጃዎች ደረጃ በደረጃና በተከታታይ ጠንከር ያሉ እንደሚሆኑ የገለጸው ባንኩ፤ ለሕግ አካላት ማሳወቅ አንዱ እንደሚሆንም አስታውቋል።

“ከሕግ አካላት ጋር በመተባበር የግለሰቦችን ስም ዝርዝር በየቅርንጫፎችና እንደሁኔታው ግለሰቦቹ ሊታወቁ በሚችሉበት አካባቢ ይፋ በማድረግ ቀጣይ ሕጋዊ እርምጃዎችን” እንደሚከተሉ አስታውቋል።

በተጨማሪም “ከፍትህ አካላትና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በመተባበር ተገቢውን የወንጀል፣ የፍትሐ ብሔር እንዲሁም አስተዳደራዊ እርምጃዎች እንዲወሰዱ እንደሚያደርግም” አሳስቧል።

የባንኩ ፕሬዝዳንት አቤ ሳኖ ረቡዕ ዕለት ለቢቢሲ ኒውስ ዴይ፣ የራሳቸው ያልሆነን ገንዘብ የወሰዱ ደንበኞች እስከ ሳምንቱ መጨረሻ ድረስ ካልመለሱ ማንነታቸውን ለፖሊስ እንደሚያሳውቁ ተናግረው ነበር።

“ማዕከሉ ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ ሲገባ 1ሺ ህፃናትን የመቀበል አቅም ይኖረዋል”
አርቲስት መቅደስ ፀጋዬ ወላጆቻቸውን በሞት ላጡ ህጻናት፣ "መቅደስ የልጆች አድማስ" የተሰኘ ማዕከል በ1 ቢሊዮን ብር ወጪ ልትገነባ መሆኑ ተገለጸ፡፡
አርቲስቷ የምታቋቁመውን የበጎ አድራጎት ድርጅት አስመልክቶ በዛሬው ዕለት በካፒታል ሆቴል ለጋዜጠኞች መግለጫ ተሰጥቷል፡፡
ድርጅቱን ለማቋቋም ሃሳቡ የተፀነሰው ከ6 ዓመታት በፊት እንደነበር አርቲስት መቅደስ ጸጋዬ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ተናግራለች፡፡
የድርጅቱ የቦርድ አባል ደራሲ ውድነህ ክፍሌ እንደገለጸው፤ ማዕከሉ በዋናነት ልዩ ትኩረትና ጥበቃ ለሚያስፈልጋቸው ወላጅ አልባ ህፃናት አስፈላጊውንና ሁሉን አቀፍ እንከብካቤ በመስጠት በቀጣይ የሕይወት ጉዟቸው ስኬታማ ይሆኑ ዘንድ ትኩረት አድርጎ የሚሰራ ነው፡፡
በማዕከሉ ውስጥ ለሚቆዩ ልጆች ደረጃውን የጠበቀ የመኖሪያ፣ የትምህርትና የጤና አገልግሎቶችን ከመስጠትና፣ የአካል ብቃት ማጎልመሻ ከማደራጀት ባሻገር፣ የማኅበራዊ ሕይወትና የአእምሮ ማበልፀጊያ ስልጠናዎችን በመስጠት ሙሉ ጤንነታቸው የተረጋገጠ፣ በአካላዊ እድገታቸው የበቁ፣ በሥነ ልቦና፣ በግልና በማሕበራዊ ሕይወታቸው ጠንካራ የሆኑ እንዲሁም በአእምሮአዊ የጠራ ችሎታቸው የተደነቁና በዕውቀት የዳበሩ ሆነው የመጪው ጊዜ ብሩህና ስኬታማ ዜጎችን እንዲሆኑ በትኩረት ይሰራል ተብሏል።
“መቅደስ የልጆች አድማስ” በማእከሉ የሚያድጉ ልጆች በሁሉም ረገድ ኢትዮጵያዊ እሴቶችን የተላበሱና አዎንታዊ ተፅዕኖ ፈጣሪዎች እንዲሆኑ ማድረግ ዋና ትኩረቱ እንደሆነ ተገልጿል።
በሃያ አንድ ሺ ካሬ ሜትር ላይ እንደሚያርፍ የተነገረለት ማዕከሉ፤ ሙሉ ለሙሉ ለመገንባትና በሙሉ አቅሙ ስራውን እንዲጀምር ለማድረግ እስከ አንድ ቢሊዮን ብር ይፈጃል ተብሏል፡፡
የበጎ አድራጎት ድርጅቱ የመጀመሪያ ማዕከሉን የሚገነባው በአዲስ አበባ ሲሆን፤ ቀስ በቀስም ወደ ከልሎች ቅርንጫፎቹን የሚያሰፋ እንደሚሆን ተነግሯል፡፡ ማዕከሉ በመጀመሪያው ዙር 200 ህፃናትን ከመላው ኢትዮጵያ የሚቀበል ሲሆን፤ ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ ሲገባ ደግሞ 1000 ህፃናትን የመቀበል አቅም እንደሚኖረው ተጠቁሟል፡፡
ማእከሉን እውን ለማድረግ መጋቢት 26 ቀን 2016 ዓ.ም በስካይላይት ሆቴል በይፋ ገቢ በማሰባሰብ ወደ ስራ የሚገባበት ቀን ሲሆን፤ በዚህ መርሃ ግብር ላይ ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች፣ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች፣ ባለሃብቶች፣ የኤምባሲ ተወካዮች፣ ታዋቂ ግለሰቦችና ሃሳቡን የሚደግፉና ቀና ልብ ያላቸው ሰዎች ይታደሙበታል ተብሏል።
• በፊልሙ ላይ 30ሺ ሰዎች ተሳትፈውበታል ተብሏል
በአርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ የተሰራውና “ስለ እናት ምድር” የተሰኘው ዶክመንተሪ ፊቸር ፊልም፣ ከነገ ወዲያ ቅዳሜ ከቀኑ 8 ሰዓት በአድዋ ድል መታሰቢያ አዳራሽ እንደሚመረቅ ተገለጸ፡፡
አርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ በዛሬው ዕለት በግዮን ሆቴል፣ ግሮቭ ጋርደን ወክ፣ ለመገናኛ ብዙኃን በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገረው፣ በፊልሙ ላይ ሰላሳ ሺ ሰዎች የተሳተፉበት ሲሆን፤ የሦስት ሰዓት እርዝማኔ እንዳለውና ታሪኩንም በሰሜኑ ኢትዮጵያ ጦርነት ላይ ያደረገ መሆኑን ጠቁሟል።
ፊልሙ በአሜሪካን ሀገር ሎሳንጀለስ ከተማ በተካሄደ የፊልም ፌስቲቫል ላይ ሁለት መቶ ከሚሆኑ ፊልሞች ውስጥ ከተመረጡ ሦስት ፊልሞች አንዱ ለመሆን እንደበቃ አርቲስት ቴዎድሮስ ለጋዜጠኞች ተናግሯል።
ፊልሙ አዲስ አበባ ከተማን ጨምሮ አላማጣ፣ ዞብል፣ ወልድያ፣ ቆቦ፣ ኮምቦልቻ እንዲሁም ጅማ ከተማና ደነባ በተሰኙ ቦታዎች ላይ የዘመኑ የመጨረሻ ቴክኖሎጂ በሆነው 12 k የተሰኘ የቪዲዮ ካሜራ እንደተቀረፀ የተገለፀ ሲሆን፤ ቀረፃውም ዓመት ከስምንት ወር እንደፈጀ ተብራርቷል።
በፊልሙ ላይ በቲክቶክ ስራዎቿ የምትታወቀው ፅጌ ሮያል መሪ ተዋናይ ስትሆን፣ አንጋፋው አርቲስት ደበበ እሸቱም ተውኖበታል ተብሏል። በዚህ ፊልም ላይ ከሆሊውድና ከቦሊውድ የመጡ ባለሙያዎችም እንደተሳተፉበት ተነግሯል፡፡
“ስለ እናት ምድር” የተሰኘው ፊልም ከምርቃቱ በኋላ በሁሉም ሲኒማ ቤቶች ለዕይታ እንደሚቀርብም ታውቋል፡፡

ሰሞኑን አዲስ አበባ እጅጉን ተዋክባለች፡፡ በተስፋና በስጋት ማዕበል እየተናጠች ነው፡፡ ተስፋው ከተማውን በማደስ ላይ በሚገኙት የመንግሥት ኃላፊዎች ፊት ላይ ሲታይ፣ ስጋቱ ደግሞ ቦታው በሚፈርስባቸው አካላትና በአልፎ ሂያጁ መንገደኛ ላይ ይስተዋላል፡፡ በተለይ ፒያሳ፣ አራት ኪሎ፣ መገናኛ፣ ቦሌና የመሳሰሉት አካባቢዎች  የነውጥና የለውጥ አየር እየነፈሰባቸው ነው፡፡ አዲስ አበባን እንደ አዲስ ለመሥራት፣ መልሶ እራሷን ለማዋለድ እየተደረገ ያለው ይህ እሽቅድምድም፣ ፍጥነቱም ክብደቱም፣ ለእኔ ቢጤው ድንገቴ ነው፡፡ አዲስ አበባችን ተዋክባለች፡፡ ሁለ ነገሯ፣ ‹አሁኑኑ ካልሆነ ሞቼ እገኛለሁ!› የምትል ሆናለች፡፡
ዘንድሮም አዲስ አበባ ለድሆች ‹ከወዲሁ ቦታችሁን ፈልጉ!› እያለች ነው፡፡ ‹ጠጋ በሉ!› እያለች ጥግ ያስያዘቻቸውና ‹ጫፍ ላይ ወራጅ አለ› ብላ ገፍትራ የጣለቻቸው ልጆቿ ቁጥር ጨምሯል፡፡ ‹እያለህ ካልሆነ ከሌለህ የለህም!› ሆኗል የዘፈን ምርጫዋ፡፡ አታስቆማቸውም፤ አታስቀምጣቸውም፤ ምናልባት  እንዲጎበኟት የመመላለሻ ፍቃድ ትሰጣቸው ይሆናል፡፡ ኮሪደሩ ግን የእነሱ አይደለም፡፡
ደግሞም ታሪክ እንደ ዘበት የተሳለማቸውና  ዘመን ያስቆጠሩ ቅርሶቿን በጥንቃቄ ሰንዳ  እንዳላስቀመጠች ያስታውቅባታል፡፡ ለእሷ አሮጌ ነገር ሁሉ አይጠቅምም፡፡
‹የገዛኸውን አዲስ ባልዲ ውሃ መያዝ አለመያዙን ሳታረጋግጥ አሮጌውን ባልዲ አትጣል!› የሚለው ብሂል ለአዲስ አበባ የሚሠራ አይመስልም፡፡
የተበጠሰው ነገር፣ ተበጥሶም እንደ አዲስ የተቀጠለው ነገር ብዙ ነው፡፡
ከእንግዲህ የምናውቃቸው ሰፈሮች እንደማናውቃቸው ሆነዋል፡፡  በነጋችን ውስጥ እነሱ የሉም፡፡ ከእንግዲህ ስማቸውና የቀደመ ምስላቸው ብቻ ነው በአንደበቶቻችን የሚደመጡት፣ በዕይታችን የሚመላለሱት፡፡ ከእንግዲህ ከላይ በተጠቀሱ ቦታዎች የተሠሩ የዘፈን ክሊፖች፣ ሥዕሎች እና ምስሎች ቅርስ ይሆናሉ፤ ከንፈር እየተመጠጡ የሚታዩ፤ ‹ለካስ ነበር እንዲህ ኖሯልና ቅርብ› የሚያስብሉ፡፡
ከእንግዲህ የዓለማየሁ ገላጋይ  ‹አጥቢያ› ልቦለድ፣ የመሀመድ ሰልማን ‹ፒያሳ ማህሙድ ጋ ጠብቂኝ› እና እነዚህን መሰል ድርሰቶች ልቦለዶች ብቻ አይደሉም፤ በራሮታዊ ስሜት የሚነበቡ መዘክሮችም ጭምር እንጂ! ሰሞኑን፣ ‹ኧረ ጎበዝ ምን እየተደረገ ነው?› ብለው ለሚጠይቁ መንግሥት፣ ‹ስጨርስ የማደርገውን ታያላችሁ› እያለ ይመስላል፡፡ እንዲህ ያለው ጉርምርምታ በፊትም ነበር፤ ወደፊትም ይኖራል፤ ነበር ይኖራልም ማለት ግን የጥያቄውን ዕድሜ ይናገራል እንጂ የአፍራሹንም የገንቢውንም ልክነት አያሳይም፡፡  ልዑል ራስ መንገሻ ሥዩም ‹የትውልድ አደራ› በሚለው መጽሐፋቸው፣ የቦሌን አይሮፕላን ማረፊያ ሜዳ ሲከልሉ ስላጋጠማቸው ችግር ሲያስታውሱ፣ ‹‹…ብዙዎቹ ጓደኞቼ የመሬቱ ባለቤቶች ነበሩ፤ መንገዱ በመቶ ሜትር ስፋት፣ አራት ኪሎ ሜትር ሲሄድ፣ የብዙዎቹን መሬት እየቆራረጠ መሄዱ አይጠረጠርም፡፡ በሀሜት መልክ ይሁን በወቀሳ መልክ ይሁን ‹ይሄ ስንዝር መሬት የሌለው ትግሬ እኮ መጥቶ ርስታችንን በሙሉ ነቀለን› የሚሉበትም ጊዜ ነበር፡፡ እኔም በዚሁ በቀልድና በዋዛ መልስ ‹አዎን ዛሬ ታለቅሳላችሁ፤ ነገ ግን የልጅ ልጆቻችሁ የሚደሰቱበት ሳይሆን አይቀርም፡፡ /…/ ላገሪቱ ደግሞ ታላቅ ሃብትና ለሕዝቡም ዕድገት ደህና መንገድ ሊሆንይችላል…እላቸው ነበር›› ብለዋል፡፡
መንግሥት አገር እየሠራሁ ነው፣ ነው የሚለው፤ ‹ከተማዋን እያበለጸግሁ!›፡፡ ለሚከፉበትም ከላይ ልዑል ራስ መንገሻ የመለሱት ዓይነት መልስ ነው የሚሰጠው፡፡
እርግጥ በፈረሱ ቦታዎች ያማሩ ነገሮች እናያለን ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፤ ሆኖም ያ ያማረ ነገር ለማየት ተብሎ ደሃ የበደለኞችና የሀብታሞች መሸጋገርያ ድልድይ እንዲሆን መፍቀድ ተገቢ አይደለም፡፡ ምን ተደረገለት ነው? ጥያቄው፡፡ አቤቱታው የት ወደቀ?
መውደቂያቸውን ሳያዘጋጁ፣ ሳይዘጋጅላቸው፣ አዋክቦ ማስወጣት ‹ምን እንዳታመጡ!› የሚል ድምጸት አለው፡፡ ይሄ ደግሞ ውጤቱ ግልጽ ነው፡፡ የተበዳይን ጩኸት የማይሰማ መንግሥት አንድም የነቃፊውን ቁጥር ያበዛል፤ አንድም የህልሙን ተጋሪ ዜጎች  በፈቃዱ ያሰናብታል፡፡
ትልቁ ነገር ሰፈር ብቻውን እንደማይፈርስ መገንዘቡ ላይ ነው፡፡ ሰፈር ቋተ ብዙ፡፡  ሰፈር መስፈርያም መሳፈርያም ነው፡፡ ራሱን በሰፈሩ ቁና የሚሰፍር ጥቂት አይደለም፡፡ በሰፈሩ ወደ ሚፈልገው ዓለም ኳትኖ የሚመለስ ተሳፋሪም ጥቂት አይደለም፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ባሉ አገራት ደግሞ ሰው የሚሠራው መጀመርያ ቤቱ ውስጥ ነው፤ ቀጥሎ ሰፈሩ፤ ቀጥሎ ቤተ እምነቱ፤ ቀጥሎ ቤተ ትምህርቱ፡፡ የሰፈሩ ግን ጥብቅ ነው፡፡ ለዚህም ነው፣ የአንድ አካባቢ ሰው ሲነሳ ጎረቤታማሞች ሳይነጣጠሉ በአንድ ሰፈር ቢሰፍሩ ይሻላል የሚባለው፤ ዕድሩም ማኅበሩም ተጠናክሮ እንዲቀጥል፡፡
አንዳንዱ እንኳንስ የተወለደበትና ያደገበት፣ የሚውልበት ሰፈር መፍረሱ ሲነገረው ሰውነቱ የመፍረስ ስሜት ይሰማዋል፡፡ ይሄ ሰውኛ ባህርይ ነው፡፡ ፈልገህ አታመጣውም፤ አስገድደህ አታባርረውም፡፡ ሰፈሩ እየፈረሰበት፣ ትልቅ ታሪካዊ ነገር ሊገነባበት ነው ሲባል፣ ነፍሱ ‹ጉሮ ወሸባዬ› እያለች አታዜምለትም፡፡ ምን ቢለወጥ፣ ምን ቢታደስ ባይነኩበት የሚመርጣቸው ጥቂት እጅግ በጣም ጥቂት ነገሮች ይኖሩታልና ሊከበሩለት ይገባል፡፡
አንድ ሰፈር በከፊልም ሆነ ሙሉ ለሙሉ ይፍረስ  ሲባል፣ ምንም ጥርጥር የለውም፣ መንግሥት ለተሻለ ነገር ቦታውን አጭቼዋለሁ ማለቱ ነው፡፡ ሰፈሩ ጨለማም፣ ኮተታም፣ የድህነት ጎተራና ማፈርያ ስለመሰለውም ጭምር ነው፡፡ ራሱን የሚያይበትና ለሌላው (በተለይ ለቀጣዩ ትውልድ) ራሱን ሊያሳይበት የሚፈልገው መስታወቱ እንዲሆን በመመኘቱ ነው፡፡  የመጣው የሄደው መንግሥት ሁሉ ማኅተሙን ከሚሰፍርባቸው ሥፍራዎች መካከል ከተሞች ዋነኛው ናቸውና እንዲህ ቢሰማው ስህተት አይሆንም፡፡
ጉዳዩ፣ የሚፈርስበት ቤተሰብ አዕምሮው እንዲዘጋጅ ተደርጓል ወይ? ነው፡፡ ምነው ቢባል የሰው ልጅ ከጊዜና ከቦታ ጋር ያለው ቁርኝት ከባድ ነው፡፡
አንዳንዱ ባይጠቀምበትም ባይጠቅመውም አሮጌ ዕቃውን አይጥለውም፤ ዕቃው ትናንትናን የሚያይበት መነጽሩ ነው፡፡ ለማንም ግልጽ እንደሚሆነው፣ ለልማት ከቦታቸው ከመነሳታቸው በፊትም ሆነ በኋላ ተነሺው ቤተሰብ አዕምሮው ዝግጁ እንዲሆን ሊደረግ ይገባል፡፡ ተከታታይ የማነቃቃት ሥራ ከተሰራ እያንዳንዱ የልማት ተነሺ ነገ ከነገ ወዲያ ወደተዘጋጀለት ስፍራ ሲያቀና አይወናበድም፡፡ እንደሰው ተቆጥሮ፣ እንደ ዜጋ ተመድቦ ወደተዘጋጀለት ስፍራ እንዲያቀና ሊጋበዝ ይገባል፡፡ በተጨማሪም፣ ቦታው ላይ ምን ዓይነት ልማት ሊከናወን እንደታሰበ በዝርዝር ቢነገረው፣ ‹ታዲያ እኔ እዚህ በመዘግየቴ ለውጡን ለምን አደናቅፈዋለሁ?› ማስባል ነበረበት፡፡
ይህ የመልሶ ማልማት እንቅስቃሴ ካለፉት ዓመታት ጀምሮ መልሶ ማድማት ሲሆን አስተውለናል፤ ብዙ ተብሎለታል፤ ከየቦታው የተነሱ ሰዎች ማኅበራዊ ሕይወታቸው ተመሳቅሎዋል፤ እሴታቸውን በግድ ተነጥቀዋል፤ ያልተገባ የካሳ ክፍያ እንዲቀበሉ ተገደዋል፤ እዳ ውስጥ ተዘፍቀዋል፡፡ ከተከበሩበት ቦታ ተነስተው ወደ ባዶነት የተሸጋገሩ፣ በዝቅተኛነት መደብ የኖሩ ብዙ ናቸው፡፡
ዜጋ ዜጋ ነው፤ አንድም ይሁን አስራ አንድ፣ ሰባ ሰባትም ሆነ ሰባት መቶ ሰባ ሰባት ያው ነው፡፡ ቁጥር አይደለም ጉዳዩ፡፡ እናም የማንም ሰብዓዊ መብት መረገጥ የለበትም፤ ማንም ለጭንቀት መዳረግ የለበትም፤ የእሱ ክፉኛ መጎዳት እኔንም ይመለከተኛል፤ ውሎዬን ያጨልመዋል ብሎ ማሰቡ ነው የሚያዋጣው፡፡
ሌላው ጉዳይ -ከምንም ነገር በላይ - እነዚህ ከየቦታው በልማት ሰበብ የተነሱ ቤተሰቦች ሰማዕታት ናቸውና በቂ ዕውቅና/ክብር ሊሰጣቸው ይገባል ብዬ እምናለሁ! ወደድንም ጠላንም እነሱ ባይነሱ፣ እነሱ ዋጋ ባይከፍሉ፣ በውድም ሆነ በግድ ተነሱ ሲባሉ እሺ ባይሉ፣ ለሁከት ቢነሳሱ የምናያቸውን ነገሮች አናያቸውም ነበር፡፡ ‹እንበለ ደም ሰማዕትነት› የሚባል ነገር አለ በሃይማኖት ትምህርት፡፡ እኔ እንደገባኝ ‹እንበለ ደም ሰማዕት› የሚባሉት በሰደፍ ባይመቱም፣ በሰይፍ ባይቀሉም ከሰማዕትነት እኩል ሊያስቆጥር የሚችል ተጋድሎ የፈጸሙ ናቸው፡፡ እነዚህ በየስፍራው በልማት ተነሺነት ተመዝግበው ኑሯቸውን የቀጠሉ፣ የሰፈሩበት ቦታ ምቹ ስሜት ያልፈጠረባቸው፣ በግድም ቢሆን ከራሳቸው ቀንሰው ሰጥተዋልና ክብር ሊሰጣቸው ይገባል፡፡
**

ሲጮሁ “ያልተሰሙት” የቤተክርስቲያን ደወሎች!

 

 


ከአዘጋጁ፡-
 እንዳለጌታ ከበደ፤  የ14 መጻሕፍት ደራሲ ሲሆን፣  ከሥራዎቹ መካከል፣ ‹ከጥቁር ሰማይ ሥር›፣ ‹ደርሶ መልስ›፣  ‹በዓሉ ግርማ ሕይወቱና ሥራዎቹ› እና  ‹ኬር  ሻዶ›.  ይጠቀሳሉ፤  የዛጎል የመጻሕፍት ባንክ መሥራች፣  የነገረ መጻሕፍት የቴሌቪዥን ፕሮግራም አዘጋጅ፤ የፎክሎርና የሥነጽሑፍ ተመራማሪም ነው፡፡

* በ36 የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናዎች 285 ሜዳልያዎች (107 የወርቅ፣ 115 የብርና 63 የነሐስ) ተገኝተዋል፤ የሻምፒዮናውን ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገቡት የኢትዮጵያ አትሌቶች ናቸዉ።
* አትሌት ቀነኒሣ በቀለ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ታሪክ 27 ሜዳልያዎችን (16 ወርቅ፣ 7ብር ና 2 ነሐስ) በመሰብሰብ ከዓለም አንደኛ ነው፡፡  በሴቶች ምድብ ደግሞ አትሌት ወርቅነሽ ኪዳኔ 21 ሜዳልያዎችን (11 የወርቅ፣ 6 የብር እና 4 የነሐስ) በመሰብሰብ ዓለምን ትመራለች፡
45ኛው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ከ2 ሳምንት በኋላ   በሰርቢያዋ ዋና ከተማ  ቤልግሬድ ላይ ይካሄዳል። በሻምፒዮናው የሚሳተፈው የኢትዮጵያ ቡድን ከ2 ሳምንት በፊት ተሰባስቦ የመጨረሻ ዝግጅቱን በአዲስ አበባና  በዙርያዋ በሚገኙት ከተሞች ሲያከናውን ቆይቷል።
ይህ የስፖርት አድማስ ዘገባ ለዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና የኢትዮጵያ ቡድን ስለሚያደርገው ዝግጅት፤ ስለ አዘጋጇ ቤልግሬድ መሠናዶ፤ ስለቀረበው የሽልማት ገንዘብ፤ ስለኢትዮጵያ ከፍተኛ የውጤት ታሪክና ስለ ዓለምአቀፍ ሻምፒዮናው አዘጋጅነት የሚዳስስ ነው።
የኢትዮጵያ ቡድን ዝግጅት
የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናው ላይ የሚሳተፈው የኢትዮጵያን ቡድን 28 አትሌቶች (14 ወንድና 14 ሴት ) ይገኙበታል። ይህን ቡድን ለመምረጥ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በጃን ሜዳ አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ የተመዘገበውን ውጤት ዋና መነሻ አድርጓል። በአገር አቀፍ ሻምፒዮናው ላይ በአዋቂና ወጣት  የውድድር መደቦች ላይ
ያሸነፉና ደረጃ ውስጥ የገቡ አትሌቶችን የሚያካትት ነው። ቡድኑን በዋና አሰልጣኝነት የሚመሩት አንጋፋው አሰልጣኝ ሁሴን ሸቦ ሲሆኑ በምክትል አሰልጣኝነት ደግሞ ቶሌራ ዲንቃ አብሯቸው ይሰራል። በኢትዮጵያ  ቡድን ዝግጅት  ከቤልግሬድ የዓየር ንብረትና መልክአ ምድር ጋር የተጣጣሙ የልምምድ መርሐግብሮችን የተከተለ ነው።  ባለፈው ሰሞን ቡድኑ ወደ ሰንዳፋ በመውጣት የመስክ ልምምድ ያከናወነ ሲሆን በትራክ ላይ መጠነኛ የፍጥነት ልምምዱን ደግሞ በኢትዮጵያ ወጣቶቹ ስፖርት አካዳሚ ሰርቷል። በሳምንቱ አጋማሽ ላይ  በአሸዋማ ስፍራ ገላን አካባቢ የቀጠለው ዝግጅት ትናንት ወደ እንጦጦ በመውጣትም ተጠናክሮ መቀጠሉን ለማወቅ ተችሏል።
ቤልግሬድ ከፍተኛ ውጤት ሊያመጣ እንደሚችል በተጠበቀው ቡድን በተለይ በወንዶች በሪሁ አረጋዊ በአዋቂ 10ኪሜ ውድድር ከፍተኛ ግምት የተሰጠው ሲሆን ቦኪ ድሪባና ታደሰ ወርቁም ከፍተኛ ተፎካካሪዎች ሆነው ተጠቅሰዋል። በሴቶች ደግሞ ለኢትዮጵያ ስኬት ግምት የተሰጣቸው በጃንሜዳውው ውድድር ያሸነፉ አትሌቶች ናቸው። የኢትዮጵያ ቡድን ባለፉት 4 ሻምፒዮናዎች  በነበረው ተሳትፎ የተቀዛቀዘውን የውጤት  የበላይነት እንደሚመልስ ተስፋ የተጣለበት ሲሆን ዘንድሮ በተለይ በአዋቂዎች ውድድር በሁለቱም ፆታዎች የራቀውን የወርቅ የሜዳልያ  በማግኘት ታሪኩን ማደሱ ይጠበቃል።
የቤልግሬድ መሠናዶ
45ኛውን የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና የምታስተናግደው  ቤልግሬድ ከ2 ዓመት በፊት የኢትዮጵያ አትሌቶች በዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ ከዓለም አንደኛ ደረጃ ይዘው የደመቁባት ከተማ ናት።
በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናው 60 በላይ አገራትን የሚወክሉ ከ500 በላይ አትሌቶችን ተሳታፊ ናቸው። ቤልግሬድ ውስጥ በሚገኘው ፍሬንድሽፕ ፓርክ ውድድሩን በብቃት የሚያስተናግድ ሲሆን አቀበት የበዛበት መሮጫው  አትሌቶችን እንደሚፈትን ተወስቷል። ሰርቢያ ከ2022 ወዲህ የዓለም አትሌቲክስ 2 ትልልቅ ውድድሮች ለማዘጋጀት የቻለች አገር ሆናለች። በ2022 እ.ኤ.አ ላይ 18ኛውን የዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮናን  በማስተናገድ በአውሮፓ አትሌቲክስ ላይ ከፍተኛ መነቃቃት ነበር የፈጠረችው።
የቤልግሬድ 24 አዘጋጅ ኮሚቴ ለሻምፒዮናው የተዘጋጁትን ሜዳሊያዎች ከሳምንት በፊት አስተዋውቋል።
“ሜዳሊያዎቹ የብረት ቁርጥራጭ ብቻ አይደሉም። በሻምፒዮናው የሚሳተፉ ተወዳዳሪዎች ሁሉ የጥረትና የትጋት ምልክት ናቸው ”በማለት ለዓለም አትሌቲክስ ማህበር ድረገፅ የተናገሩት የኮሚቴው ፕሬዝዳንት ስሎቦዳን ብራንኮቪች ናቸው። የሰርቢያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ከሻምፒዮናው በፊት በአለም እና በአውሮፓ ደረጃ  ውድድሮችን በብቃት ማዘጋጀቱን በመጥቀስ ከሜዳሊያ ዲዛይን አንስቶ በመስተንግዶ ብቃት ልዮና የተዋጣለት ሻምፒዮና  እንዲሆን  እንፈልጋለንንም ብለዋል።
310ሺ ዶላር የገንዘብ ሽልማት
የዓለም አትሌቲክስ ማህበር ለሻምፒዮናው በድምሩ ከ310 ሺ ዶላር  በላይ የሽልማት ገንዘብ ያዘጋጃል፡፡  በግልና በቡድን  ከ1ኛ እስከ 6ኛ ደረጃ ለሚያገኙ አትሌቶች የሽልማት ገንዘቡ ይከፋፈላል፡፡ በአዋቂ አትሌቶች የሁለቱም ፆታዎች የውድድር መደቦች በግል  ውጤት ለሚያስመዘግቡ አትሌቶች ለ1ኛ 30ሺ ዶላር፣ ለ2ኛ 15ሺ ዶላር፣ ለ3ኛ 10ሺ ዶላር፣ ለ4ኛ 7ሺ ዶላር፣ ለ5ኛ 5ሺ ዶላር እንዲሁም ለ6ኛ ደረጃ 3ሺ ዶላር ይበረከታል፡፡ በቡድን ውጤት ለሚያሸንፉ አገራት ደግሞ ለ1ኛ 20ሺ ዶላር፣ ለ2ኛ 16ሺ ዶላር፣ ለ3ኛ 12ሺ ዶላር፣ ለ4ኛ 10ሺ ዶላር፣ ለ5ኛ 8ሺ ዶላር እንዲሁም ለ6ኛ ደረጃ 4ሺ ዶላር የሚታሰብ ሲሆን በሁለቱም ፆታዎች ድብልቅ የዱላ ቅብብል ውድድር ለ1ኛ 12ሺ ዶላር፣ ለ2ኛ 8ሺ ዶላር፣ ለ3ኛ 6ሺ ዶላር፣ እንዲሁም ለ4ኛ 4ሺ ዶላር እንደሚሸለም ታውቋል፡፡ የኢትዮጵያ አትሌቶች ከፍተኛ ውጤትና አዘጋጅነቱ ወደፊት
ኢትዮጵያ ከቤልግሬድ በፊት  ከተከናወኑት 44 የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናዎች በ36 ለመካፈል በቅታለች። የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና የስታትስቲክስ መፅሐፍ እንደሚያለክተው ኢትዮጵያ በተሳተፈችባቸው 36 የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናዎች 285 ሜዳልያዎች (107 የወርቅ፣ 115 የብርና 63 የነሐስ) በማግኘት በከፍተኛ ውጤት  ከዓለም ሁለተኛ ደረጃ ላይ ናት።
የኢትዮጵያ አትሌቶችም በሻምፒዮናው ታሪክ ከፍተኛውን የሜዳልያ ስብስብ በማግኘት ግንባር ቀደም ናቸው፡፡ አትሌት ቀነኒሣ በቀለ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ታሪክ 27 ሜዳልያዎችን (16 ወርቅ፣ 7ብር ና 2 ነሐስ) በመሰብሰብ ከዓለም አንደኛ ነው፡፡  በሴቶች ምድብ ደግሞ አትሌት ወርቅነሽ ኪዳኔ 21 ሜዳልያዎችን (11 የወርቅ፣ 6 የብር እና 4 የነሐስ) በመሰብሰብ ዓለምን ትመራለች፡፡
የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና  በኢትዮጵያ   ታላላቅ ውጤቶች የተመዘገበበት ውድድር ከመሆኑም  በላይ  በኦሎምፒኮችና በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች ታላላቅ ስኬት ያገኙ አትሌቶችም    ተገኝተውበታል፡፡
ይህ ታሪክ ውድድሩን በኢትዮጵያ ለማስተናገድ ምክንያት መሆን አለበት።
የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናው በማዘጋጀት የአውሮፓና የአፍሪካ አገራት ከፍተኛ ድርሻ ይወስዳሉ።
በአፍሪካ እህጉር ሻምፒዮናው ለሶስት ጊዜያት ተዘጋጅቷል፡፡ ከ7 ዓመት በፊት የሻምፒዮናውን አዘጋጅነት የምስራቅ አፍሪካዋ ኡጋንዳ አግኝታ በተሳካ ሁኔታ ማስተናገዷ የሚታወስ ሲሆን ከዚያ በፊት በ1998 በማራካሽ ሞሮኮ እንዲሁም በ2007 እኤአ በሞምባሳ ኬንያ ሻምፒዮናው ተካሂዷል፡፡ በ2026 እኤአ ላይ 46ኛውን የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና በአሜሪካ ታሀላሴ እንዲካሄድ ተወስኗል። በአፍሪካ አህጉር ለ4ኛ ጊዜ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናውን በ2028 ወይንም በ2030 ለማዘጋጀት የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን መስራት ይኖርበታል፡፡
የዓዎች አገር አቋራጭ ሻምፒዮናው ከመላው ዓለም  ከ140 በላይ ሚዲያዎች በስፍራው ተገኝተው የሚዘግቡትና በዓለም አቀፍ የቲቪ ስርጭት ከ5 ሚሊዮን በላይ ተመልካቾችን የሚያገኝ ነው።፡
 በዋናዎቹ ውድድሮችና ሌሎች መርሃ ግብሮች ከ2ሺ በላይ ተሳታፊዎች ያሉት ሲሆን ከመላው ዓለም ተሰባስበው አዘጋጅ ከተማ ድረስ የሚገኙ ከ10ሺ በላይ የአትሌቲክስ አፍቃሪዎአ ናቸው።  ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ማህበር በሰራው ጥናት የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናውን ለማዘጋጀት አስፈላጊውን የመወዳደርያ ስፍራና የስፖርት መሰረተልማቶች ከማሟላት ባሻገር እስከ 2.3 ሚሊዮን ዶላር በጀት መመደብን ይጠይቃል፡፡     ከስታድዬም የመግቢያ ትኬቶች፤ ከስፖንሰርሺፕ እና ከሚዲያ መብት በአጠቃላይ ከ 3.07 ሚሊዮን ዶላር በላይ በቀጥታ ገቢ ይሆንበታል።

Page 8 of 703