ከፍተኛው የሆቴሎች ዋጋ ጭማሪ የታየው በሻርም አል ሼክ ነው

   ኤስ ቲ አር ግሎባል የተባለው አለማቀፍ የጥናት ተቋም በተለያዩ የአፍሪካ አገራት ከተሞች የሆቴሎች ዋጋ ዙሪያ ባደረገው ጥናት፤ አዲስ አበባ በሆቴሎች ዋጋ ውድነት ቀዳሚውን ደረጃ መያዟን ትናንት ባወጣው ሪፖርት መግለጹ ተዘገበ፡፡
ተቋሙ ይፋ ባደረገው የጥናት ውጤት፤ ባለፉት ስድስት ወራት በአዲስ አበባ ሆቴሎች ለአንድ መኝታ ክፍል ለአንድ ቀን አዳር በአማካይ 231.78 ዶላር ሲከፈል መቆየቱን ጠቁሞ፤ ይህም የከተማዋ ሆቴሎች ዋጋ ከሌሎች የአፍሪካ ሆቴሎች የበለጠና እጅግ ውዱ መሆኑን እንደሚያሳይ ጋና ቢዝነስ ኒውስ ድረገጽ ዘግቧል፡፡
የናይጀሪያዋ ሌጎስ 215.75 ዶላር፣ የኬንያዋ ናይሮቢ 144.76 ዶላር፣ የደቡብ አፍሪካዋ ኬፕታውን 122.30 ዶላር ለአንድ አዳር በማስከፈል እስከ አራተኛ ያለውን ደረጃ መያዛቸውንም ዘገባው ጠቁሟል፡፡የአገሪቱ ኢኮኖሚ ላለፉት አስር ያህል አመታት በአማካይ ከ10 በመቶ በላይ ዕድገት ማስመዝገቡ፣ የተለያዩ አለማቀፍ ጉባኤዎችን ማስተናገዷ፣ የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ መሆኗ እና በእድገት ላይ የሚገኘው የኢትዮጵያ አየር መንገድ የመዳረሻዎቹንና የተሳፋሪዎቹን ቁጥር ማሳደጉ፣ በአገሪቱ የዘመናዊ ሆቴሎች ፍላጎት እንዲጨምር አድርጓል ያለው ጥናቱ፣ ይሄም ሆኖ ግን አዲስ አበባ አሁንም ድረስ ከፍተኛ የጥራት ደረጃ ያላቸው ሆቴሎች እጥረት አለባት ብሏል፡፡ባለፉት 12 ወራት በአፍሪካ የተለያዩ ከተሞች የታዩ የሆቴሎች ዋጋ ጭማሪዎችን የዳሰሰው ጥናቱ፣ በተጠቀሰው ጊዜ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ የታየው በግብጹ የመዝናኛ ስፍራ ሻርም አል ሼክ መሆኑን ጠቁሞ፣ የዋጋ ጭማሪውም 42.5 በመቶ እንደሆነ ገልጿል፡፡በተጠቀሰው ጊዜ በሆቴሎች ዋጋ ላይ አዲስ አበባ የ14.9 በመቶ፣ ጆሃንስበርግ የ11 በመቶ፣ ኬፕታውን የ10.8 በመቶ ጭማሪ ማድረጋቸውንና በአንጻሩ ግን የካዛብላንካ ሆቴሎች ዋጋ በ4 በመቶ ቅናሽ ማሳየቱን አስታውቋል፡፡

Published in ዜና

ለበዓሉ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉ ነጋዴዎች ላይ የማያዳግም እርምጃ ይወሰዳል ተባለ
ኤልፎራ ከ30ሺ በላይ ዶሮና ከ1 ሚሊዮን በላይ እንቁላል ለገበያ አቅርቧል
       በርበሬ በህገወጥ መንገድ ከአገር እየወጣ መሆኑ የተጠቆመ ሲሆን ይህም ለበርበሬ ዋጋ መናር ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንዳለው ተገለፀ፡፡ የንግድ ውድድርና የሸማቾች ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ መርከቡ ዘለቀ ከአዲስ አመት በዓል ግብይት ጋር በተያያዘ ትናንት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ  እንደተናገሩት፤ የበርበሬ ምርት ዋጋ መናርን አስመልክቶ በተደረገ ጥናት፣ ምርቱ በደቡብና በሰሜን የበርበሬ አምራች በሆኑ አካባቢዎች በሚገኙ ደላሎች አማካኝነት በህገወጥ መንገድ በድንበር ሾልኮ እንዲወጣ እየተደረገ መሆኑ ታውቋል፡፡ በህጋዊ መንገድ እሴት እየተጨመረበት ወደ ውጭ አገር ተልኮ የውጭ ምንዛሬ ከሚያስገኘው የበርበሬ ምርት በተጨማሪ በህገወጥ መንገድ በደላሎችና በህገወጥ ነጋዴዎች ከአገር እንዲወጣ በመደረግ ላይ ያለው የበርበሬ ምርትም የዋጋ መናሩን  ብለዋል፤ ዳይሬክተሩ፡፡
የበርበሬ ምርትን አስመልክቶ ጥናት መደረጉን የጠቆሙት አቶ መርከቡ፤ ባለፉት 3 ዓመታት ምርቱ እየቀነሰ መምጣቱን ጠቅሰው ዘንድሮ የተመረተው 1.7 ሚሊዮን ኩንታል በርበሬ ከዓምናው ጋር ሲነፃፀር በ834ሺ ኩንታል ያነሰ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ የምርቱ ማነስም ለዋጋ ንረቱ መባባስ ምክንያት እንደሆነም ዳይሬክተሩ አስረድተዋል፡፡
በህገወጥ መንገድ ከአገር እየወጣ ነው የተባለውን የበርበሬ ምርት ለመቆጣጠር የሚያስችል የንግድ ሚኒስቴርና የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ሠራተኞች የተካተቱበት ፀረ ኮንትሮባንድ ኮሚቴ ተቋቁሞ፣ የበርበሬ አምራች በሆኑ አካባቢዎች ላይ ጥብቅ ቁጥጥርና ክትትል እየተደረገ እንደሆነም ተገልጿል፡፡
መጪውን የአዲስ አመት በዓል ምክንያት በማድረግ ህብረተሰቡ በሚፈልጋቸው ምርቶች ላይ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉ ነጋዴዎች ላይ የማያዳግም ጥብቅ እርምጃ ለመውሰድ ዝግጅት መደረጉን የገለፁት አቶ መርከቡ፤ እርምጃው ሱቆችን ማሸግና ንግድ ፈቃድን እስከመሰረዝ እንደሚደርስ አስታውቀዋል - እንደ ቀድሞው ለማወያየትና ለይቅርታ ጊዜ እንደማይሰጥ በመጠቆም፡፡ መንግስት ገበያውን ለማረጋጋትና ህብረተሰቡ የሚፈልጋቸውን ሸቀጦች በስፋት ለማቅረብ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ እንደሆነ የተገለፀ ሲሆን አቅም ያላቸው ነጋዴዎችም ገበያውን ለማረጋጋት የበኩላቸውን ሚና እንደሚጫወቱ ተነግሯል፡፡
 ኤልፎራ ለበዓሉ ገበያ ከ30ሺ በላይ ዶሮዎችንና ከአንድ ሚሊዮን በላይ እንቁላሎችን እንዳቀረበ ዳይሬክተሩ ተናግረዋል፡፡ ለገበያ በሚቀርቡ ምርቶች ላይ አላስፈላጊ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉና ትክክለኛውን የገበያ ሥርዓት ለማደናቀፍ በሚሞክሩ ነጋዴዎች ላይ ለሚወሰደው እርምጃ፣ ህብረተሰቡ ሊተባበርና ህገወጦችን በመጠቆም፣ ከመንግስት ጐን ሊቆም እንደሚገባም ዳይሬክተሩ አሳስበዋል፡፡   

Published in ዜና

    ኢትዮጵያን ጨምሮ የተለያዩ ሃገራትን በተለዋዋጭ የአየር ሁኔታና የዝናብ እጥረት እንዲጠቁ ያደረገው የዘንድሮው የኤሊኖ ክስተት ከ50 አመት ወዲህ ከታዩ 4 ተመሳሳይ ክስተቶች የከፋ ነው ተብሏል፡፡ የአለማቀፉ የሜትሮሎጂ ድርጅት ትንበያን ጠቅሶ ቢቢሲ እንደዘገበው፤ ኢትዮጵያን ጨምሮ በተለያዩ የአለም ክፍሎች ላይ የአየር መዛባት ተከስቷል፡፡ ኢሊኖ የውቅያኖስ መቀት መጨመርን ተከትሎ የሚፈጠር የአየር መዛባት መሆኑን የጠቆመው ሪፖርቱ፤ በተለይ የዘንድሮው የፓስፊክ ውቅያኖስ ሙቀት መጨመር በታሪክ ጠንካራውን የኤሊኖ ክስተት አለም እንድታስተናግድ አስገድዷል ብሏል፡፡
ከዚህ ቀደም ጠንካራ የአየር መዛባት ተከስቶ የነበረው እ.ኤ.አ ከ1997-98 መሆኑን ጠቅሶ “የዘንድሮው ክስተት ከዚያም የከፋ ነው፤ ከ1990ዎቹ ወዲህ ታይቶ የማይታወቅ አይነት ነው” ብሏል ቢቢሲ በዘገባው፡፡
ክስተቱ ባጋጠመባቸው ሃገራት በሚቀጥሉት ወራት ተመጣጣኝና በቂ የዝናብ ስርጭት ሊኖራቸው እንደሚችልም የትንበያ ሪፖርቱ አመልክቷል፡፡ በቀጣይ የሚኖረው የአየር ፀባይ፣ የኤስያ ሃገራትን በድርቅ ሊያስመታ በሰሜን አሜሪካ ከባድ ጐርፍ የሚያስከትል ዝናብ ሊከሰት ይችላል ተብሏል፡፡
ኢትዮጵያ በምትገኝበት የምስራቅ አፍሪካ አካባቢም በጐርፍ የሚያጥለቀልቅ ዝናብ ሊፈጠር እንደሚችልና በአንፃሩ በደቡባዊ የአፍሪካ ክፍል ድርቅ ሊያስከትል የሚችል የዝናብ እጥረት እንደሚኖር ከትንበያው መረዳት ተችሏል፡፡
በኢትዮጵያ እየተገባደደ ባለው የክረምት ወራት፣ ሰብል አብቃይና ቆላማ በሆኑ የሀገሪቱ አካባቢዎች ካለፉት አመታት አንፃር ድርቅን ያስከተለ ከፍተኛ የዝናብ እጥረት መፈጠሩ የሚታወስ ሲሆን በተለይ በአፋር የአደጋው መጠን የቤት እንስሳትን ለሞት እስከመዳረግ ደርሷል፡፡ መንግስት በበኩሉ፤ በአየር መዛባት ምክንያት ባጋጠመው የዝናብ እጥረትና መቆራረጥ 4.5 ሚሊዮን ዜጐች እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው ገልጿል፡፡
በሀገሪቱ ሰኔና ሐምሌ ዝናብ አጥተው የነበሩ አካባቢዎችም በነሐሴ የተሻለ የዝናብ ስርጭት እንደነበራቸው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሜቲዎሮሎጂ ኤጀንሲ ገልፆ እንደነበር የሚታወስ ሲሆን በሀረር፣ ድሬደዋ፣ ደብረብርሃን፣ ወሎና አፋር አካባቢዎች ላይ ሰሞኑን ዝናብ እየዘነበ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡

Published in ዜና

      ከተከሰሱበት የሽብር ክስ ፍ/ቤት በነፃ ያሰናበታቸውን የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር አቶ ሀብታሙ አያሌውን ማረሚያ ቤቱ ለምን ከእስር እንዳልለቀቃቸው ፍ/ቤት ቀርቦ ያስረዳ ሲሆን ጉዳዩን  የተመለከተው ችሎት፤ ተከሳሽ እስከ ይግባኝ ቀጠሮ ድረስ በማረሚያ ቤት እንዲቆዩ ትዕዛዝ ሰጠ፡፡
ተከሳሹ ነሐሴ 27 ቀን 2007 ዓ.ም ለፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት የፃፉትን አቤቱታ መሰረት አድርጎ ነበር ችሎቱ በትናንትናው እለት ተከሳሹና የማረሚያ ቤት ኃላፊዎች ቀርበው ስለ ጉዳዩ እንዲያስረዱ ያዘዘው፡፡
አቶ ሀብታሙ ለችሎቱ በፅሁፍ ባቀረቡት አቤቱታ፤ ነሐሴ 14 ቀን 2007 ዓ.ም ጉዳያቸውን ሲመረምር የነበረው ፍ/ቤት፣ በነፃ እንዳሰናበታቸው ጠቅሰው ማረሚያ ቤቱ ከእስር ሊለቃቸው ያልቻለበትን ምክንያት ፍ/ቤት ቀርቦ እንዲያስረዳላቸውና አስፈላጊውን እርምጃ እንዲወስድላቸው ጠይቀው ነበር፡፡
በትናንትናው እለት ተረኛ ችሎት የቀረቡት የማረሚያ ቤቱ ተወካይ ኃላፊ፤ ተከሳሹ በማረሚያ ቤት እንዲቆዩ የተደረገው የጠቅላይ ፍ/ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ትዕዛዝን በማክበር ነው ሲሉ አስረድተዋል፡፡
“ተከሳሹ አቶ ሀብታሙ በማረሚያ ቤት እንዲቆዩ የተደረገው፣ በነፃ በተሰናበቱ ማግስት አቃቤ ህግ ይግባኝ በመጠየቁና ይግባኝ ሰሚ ችሎቱ፣ ተከሳሹ እስከ ይግባኝ ቀጠሮ ጥቅምት 21 ቀን 2008 ዓ.ም በማረሚያ ቤት እንዲቆዩ ትዕዛዝ በማስተላለፉ ነው” ብለዋል - የማረሚያ ቤቱ ተወካይ ኃላፊ፡፡ በተጨማሪም ይግባኝ ሰሚ ፍ/ቤቱ በከፍተኛው ፍ/ቤት የተደረገው ክርክር ግልባጭ እንዲቀርብ ማዘዙን ኃላፊው ጠቁመዋል፡፡ ተከሳሹ አቶ ሀብታሙ በበኩላቸው፤ ከፍተኛው ፍ/ቤት በነፃ ካሰናበታቸው በኋላ ለምን ታስረው እንደቆዩ እንዲገለፅላቸው የአስተዳደር አካላትን በደብዳቤም ጭምር መጠየቃቸውን ጠቁመው ኃላፊዎቹን ግን “መልስ ለመስጠት አንገደድም” በሚል ምክንያቱን ሳያስረዱኝ ቀርተዋል፤  ያልተፈታሁበት ምክንያት ለኔም ሆነ ለቤተሰቤ ባለመገለፁ፣ ቤተሰቦቼ ላይ ከፍተኛ እንግልት ደርሷል” ሲሉ ቅሬታቸውን ሰንዝረዋል፡፡
“ቤተሰቦቼ እኔን ለማስፈታት በመጡ ጊዜ እስከ ምሽት ድረስ ይፈታል ጠብቁ ተብለው ተንገላተዋል” ብለዋል - ተከሳሹ ለችሎቱ፡፡
የማረሚያ ቤቱ ተወካይ ኃላፊ በበኩላቸው፤ ተከሳሹ ያልተፈቱበት ምክንያት ተገልፆላቸዋል፤ ከቤተሰብ አካላት በጉዳዩ ላይ ጥያቄ ያቀረበ ግን የለም ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
በመጨረሻም ያህል ጉዳዩን መርምሮ ብይን የሰጠው ፍ/ቤቱ፤ ተከሳሹ በማረሚያ ቤት እንዲቆዩ የተደረገበት ምክንያት ከማስረጃ ጋር የተደገፈና በቂ ማብራሪያ የቀረበበት በመሆኑ፤ በማረሚያ ቤት ቆይተው ጉዳያቸውን በጠቅላይ ፍ/ቤት ወንጀል ይግባኝ ሰሚ ችሎት እንዲከታተሉ ብይን ሰጥቷል፡፡
የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበሩት አቶ ሀብታሙ አያሌውን ጨምሮ በእነ ዘላለም ወ/አገኘሁ የክስ መዝገብ በሽብር ከተከሰሱት 10 ግለሰቦች መካከል አምስቱ በነፃ እንዲሰናበቱ ከፍተኛ ፍ/ቤት ነሐሴ 14 ቀን 2007 ዓ.ም ብይን መስጠቱ ይታወሳል፡፡

Published in ዜና

ንግድ ባንክ የአስቀማጭ ደንበኞች ቀንን የፊታችን ማክሰኞ የሚያከብር ሲሆን በ”ይቆጥቡ ይሸለሙ” የተሸለሙ የአዲስ አበባ እድለኞች በእለቱ ሽልማታቸውን ይረከባሉ፡፡
ባንኩ የአስቀማጭ የደንበኞች ቀንን ለ4ኛ ጊዜ የሚያከብር ሲሆን የባንኩ የቦርድ አባላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንዲሁም ተሸላሚዎች ይታደማሉ ተብሏል፡፡ ፕሮግራሙ ከ11 ሰዓት ጀምሮ በሂልተን ሆቴል ቦልሩም አዳራሽ እንደሚካሄድ የጠቆመው ባንኩ፣ የ4ኛ ዙር “የይቆጥቡ ይሸለሙ” ፕሮግራምና 1ኛ ዙር የወጭ ምንዛሬ ግኝት ማበረታቻ ፕሮግራም ላይ አሸናፊ የሆኑ የአዲስ አበባ ዲክትሪክት እድለኞችም ሽልማታቸውን ይረከባሉ፡፡ ቀደም ሲል ባንኩ በሁለቱም የሽልማት ፕሮግራሞቹ ከ2 ሺህ በላይ አሸናፊዎችን ስም ዝርዝር ይፋ ማድረጉ የሚታወስ ነው፡፡ ቁጠባን ለማበረታታት ባንኩ ባለፉት አራት የ “ይቆጥቡ ይሸለሙ” ዙር ፕሮግራሞች በርካቶችን ተጠቃሚ ማድረጉንና ቆጣቢ ደንበኞችንም እያበራከተ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡

Published in ዜና

   ከአዲስ አበባ 17 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው የሰበታ ከተማ ነዋሪ የሆኑ ከ500 በላይ አባወራዎች፤ ከ7 አመታት በላይ በመብራትና ውሃ እጦት መሰቃየታቸውን በምሬት ተናገሩ፡፡
በሰበታ ከተማ ቀበሌ 08 ጐጥ 9 በሚባል አካባቢ ነዋሪ እንደሆኑ የገለፁት አቤቱታ አቅራቢዎቹ፤ ዋና ችግራቸው የመብራት፣ የውሃና የመንገድ መሠረተ ልማት አቅርቦት መሆኑን ይናገራሉ፡፡
ከ4 አመት በፊት ከመንግስት ጋር በመተባበር መብራት፣ ውሃና መንገድ ለማሠራት እያንዳንዱ አባወራ 2500 ብር ማዋጣቱን ያስታወሱት አባወራዎቹ፤ አሁንም ድረስ ግን ምንም የተሟላላቸው ነገር እንደሌለ ገልፀዋል፡፡
“መንግስት በተቻለው አቅም በተለይ ለመብራት መሠረተ ልማት የሚያገለግሉ ቁሳቁሶችንና ሠራተኞችን እየላከልን ነው” የሚሉት ነዋሪዎቹ፤ ችግሩ ያለው የከተማ አስተዳደሮቹ ጋ ነው ብለዋል፡፡ “የከተማ አስተዳደሩ እኛን እንደተቀረው የከተማ ነዋሪ አይመለከተንም፤ አጠገባችን ባሉ መንደሮች መብራትና ውሃ እያለ እኛ ጋ ግን የለም” ያሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ በተደጋጋሚ ለሚያቀርቡት የልማት ጥያቄ ቀና ምላሽ እንደማይሠጣቸውም ይናገራሉ፡፡
በመንግሥት ገንዘብ በውድ ዋጋ ተገዝተው ለአገልግሎት እንዲውሉ የተላኩ የኤሌክትሪክ ገመዶችና ቋሚ ምሰሶዎች በከንቱ ሜዳ ላይ እየባከኑ ነው ሲሉም ተናግረዋል፤ ነዋሪዎቹ፡፡
የኤሌክትሪክ ኃይል ዝርጋታው ለምን ዘገየ የሚል ጥያቄ ስናቀርብ ሁሌም የትራንስፎርመር አቅርቦት ችግር በምክንያትነት ይጠቀሳል ያሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ሶስት ትራንስፎርመር ለዚሁ ተብሎ ተገዝቶ እንደተቀመጠ ግን እናውቃለን ይላሉ፡፡
ከትናንት በስቲያ ከሰበታ ተነስተው አዲስ አበባ ወደሚገኘው የኦሮሚያ ውሃና ኢነርጂ ቢሮ ተሠባስበው በመሄድ አቤቱታ ማቅረባቸውን ለአዲስ አድማስ የተናገሩት አባወራዎቹ፤ የቢሮው ተወካይ ሃላፊም ወደ ከተማ አስተዳደሩ ባለስልጣናትና የሚመለከታቸው አካላት ዘንድ ስልክ በመደወል፣ በተለይ የመብራት አገልግሎቱ እስከመቼ እንደሚጠናቀቅ ጠይቀው፣ በሁለት ወር ጊዜ ውስጥ ይጠናቀቃል የሚል ምላሽ ማግኘታቸውን ነግረውናል ብለዋል፡፡  የውሃ ጥያቄያቸውም በከተማ አስተዳደሩ በኩል ምላሽ እንደሚያገኝ ተገልፆላቸዋል፡፡

Published in ዜና

የሜዲካል ቱሪዝም መዳረሻ አገራት በየዓመቱ ከ100 ቢ. ዶላር በላይ ገቢ ያገኛሉ
    በግራ እግሩ ጣቶች ላይ የጀመረው የህመም ስሜት እያደር እየበረታና እየጠነከረ መሄዱ ቢሰማውም እንዲህ ለከፋ ደረጀ ያደርሰኛል ብሎ ለአፍታም አስቦ አያውቅም፡፡ ከዛሬ ነገ ይሻለኛል እያለ ስሜቱን ችላ ቢለውም ህመሙ ዕለት ከዕለት እየጨመረ መሄዱ አሳሰበው፡፡ ሁኔታው ሲከፋበትም ወደ ሃኪም ዘንድ ሄደ፡፡ በሽታውን የመረመሩት ሃኪሞች የተለያዩ መድሃኒቶችን በማዘዝ፣ ህመሙን ለማስታገስና ከበሽታው ለመፈወስ ጥረት ቢያደርጉም በቀላሉ ሊሳካለቸው አልቻለም፡፡ ከብዙ ውጣ ውረድና ድካም በኋላ በሽታው የአጥንት ካንሰር መሆኑንና ህክምናውም እዚህ አገር እንደማይሰጥ ነግረው፣ ወደ ውጪ አገር ሄዶ እንዲታከም ፃፉለት፡፡ ለ32 ዓመቱ ወጣት ዳዊት ተስፋዬ ነገሩ ዱብዕዳ ነበር፡፡ ድንጋጤው መለስ ሲልለት ስለ ህክምናው ሁኔታና ህክምናው ስለሚሰጥባቸው አገራት መረጃ ማሰባሰብ ጀመረ፡፡ ታይላንድ፣ ሲንጋፖር፣ ህንድ፣ ቻይናና ደቡብ አፍሪካ ውስጥ ላሉ የህክምና ተቋማት በኮሚሽን የሚሰሩ ኤጀንሲዎችን አግኝቶ ለህክምናው የሚያስፈልገውን የገንዘብ መጠን ማጠያየቅ ያዘ፡፡ በመጨረሻም ለህክምናው ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ እንደሚያስፈልገው ተነገረው፡፡ ገንዘቡ ከአቅሙ በላይ በመሆኑም ዋጋ ያወጡልኛል ያላቸውን ንብረቶቹን በመሸጥና ወዳጅ ዘመዶቹ የእርዳታ እጃቸውን እንዲዘረጉለት በመጠየቅ፣ ገንዘብ የማሰባሰቡን ተግባር ተያያዘው፡፡ ከተሳካለትም በመጪው አዲስ አመት መጀመሪያ ላይ በአንፃራዊነት የተሻለ ዋጋ ወደቀረበለት ህንድ ተጉዞ ህክምናውን ለማድረግ ዕቅድ ይዟል፡፡ እንዲህ እንደ ዳዊት በተለያዩ በሽታዎች የተያዙ በርካታ ዜጐች ህክምና ለማግኘት ወደ ታይላንድ፣ ቻይና፣ ሲንጋፖር፣ ህንድ፣ ደቡብ አፍሪካና ሌሎች የአውሮፓ አገራት ይጓዛሉ፡፡ የህክምና አገልግሎትን ለማግኘት ከአገር አገር ድንበር አቋርጦ የሚደረገው ጉዞም የህክምና (ሜዲካል) ቱሪዝም ተብሎ ይጠራል፡፡ የህክምና ቱሪዝም አገራት እጅግ ከፍተኛ ገቢ የሚያገኙበት የቱሪዝም ዘርፍ ሆኗል፡፡ ሜዲካል ቱሪስቶች ጉዞአቸውን የሚያደርጉባቸው ምክንያቶች ሊለያዩ ይችላሉ፡፡ አብዛኛውን ጊዜ የሚሹትን ህክምና በአገራቸው ለማግኘት ያልቻሉ ሰዎች ህክምና ፍለጋ ወደ ሌሎች አገራት የሚንቀሳቀሱ ቢሆንም ዝቅተኛ የህክምና ክፍያ ፍለጋ አሊያም ወረፋ ላለመጠበቅ ህክምናውን በፍጥነት ወደሚያገኙባቸው ሌሎች አገራት የሚንቀሳቀሱ ሜዲካል ቱሪስቶችም አሉ፡፡ በርካቶች ለህክምና ከሚመርጧቸው የሜዲካል ቱሪዝም መዳረሻ አገራት መካከል ብዙዎቹ በደቡብ ምሥራቅ እስያ ውስጥ የሚገኙ ሲሆኑ ጥቂት የአውሮፓ አገራትና ደቡብ አፍሪካም በሜዲካል ቱሪዝም መዳረሻነታቸው የሚጠቀሱ አገራት ናቸው፡፡ አንዳንድ አገራትም በዓለማችን የተለያዩ አገራት ውስጥ ወኪሎቻቸውን አስቀምጠው የሜዲካል ቱሪስት ፍለጋውን እያጧጧፉት እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
የዓለም ጤና ድርጅት ያወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ የሜዲካል ቱሪዝም ዓለም አቀፍ ገበያ
በዓመት ከ100 ቢሊየን ዶላር በላይ ነው፡፡ በዓለማችን ህክምና ፈላጊ ቱሪስቶችን የሚያስተናግዱ አገራት ቁጥር 40 እንደሚደርስ የጠቆመው መረጃው፤ ህንድ፣ ብራዚል፣ ሲንጋፖር፣ ታይላንድ፣ ቻይና፣ ሀንጋሪ፣ ኮስታሪካ፣ ማሌዥያ፣ ሜክሲኮና ደቡብ አፍሪካ ዋንኛ የሜዲካል ቱሪዝም መዳረሻ አገራት መሆናቸውን ገልጿል፡፡ እነዚህ አገራት እጅግ ከፍተኛ ዶላር በሚዝቁባቸው በልብ ቀዶ ጥገና፣ በአካል ንቅለ ተከላ፣ ውስብስብ በሆኑ የአጥንቶችና የመገጣጠሚያ ህክምናዎች፣ በጥርስ ህክምና፣ በካንሰር ህመሞች ህክምናና በፊት ቀዶ ህክምናዎች የተራቀቁ ናቸው፡፡ ከዋና ዋናዎቹ የሜዲካል ቱሪዝም መዳረሻ አገራት መካከል አንዳንዶቹ ህመምተኞቻቸውን በአነስተኛ ዋጋ በማስተናገድ የሜዲካል ቱሪዝም የበለጠ የሚስፋፋባቸውን መንገዶች ሲፈልጉ ይስተዋላሉ፡፡ከእነዚህ አገራት ደግሞ ህንድ ቀዳሚነቱን ትይዛለች፡፡ ከልብ ጋር ለተያያዙ ህክምናዎች፣ ለሽንጥና ለመገጣጠሚያ ችግሮች ብዙዎች የሚመርጧት ህንድ፤ ረቀቅ ያሉ መሳሪያዎችንና ጥልቅ ዕውቀትን ለሚጠይቁት የህክምና አገልግሎት የምታስከፍለው ገንዘብ በአሜሪካና በእንግሊዝ ለተመሳሳይ ህክምና ከሚጠየቀው ገንዘብ አንድ አስረኛውን ብቻ ነው፡፡ የህንድ የጤና ከተማ እየተባለች
የምትጠራውና የደቡባዊዋ ህንድ ከተማ ቼናይ፣ ከተለያዩ የዓለማችን አገራት ጤናቸውን ፍለጋ የሚጓዙ በርካቶችን ታስተናግዳለች፡፡ 45 በመቶ የሚደርሱ ዓለም አቀፍ ታካሚዎችም ከደዌአቸው ለመፈወስ ይህችኑ ከተማ የሙጢኝ ብለዋል፡፡ አገሪቱ ከሜዲካል ቱሪዝም ዘርፍ የምታገኘው ዓመታዊ ገቢ ከ3 ሚሊዮን ዶላር በላይ እንደሚሆን የዓለም ጤና ድርጅት መረጃ ያመላክታል፡፡ ህንድ በመላው ዓለም ከሚገኙና የሜዲካል ቱሪዝም መዳረሻ ከሆኑት አገራት መካከል በአንፃራዊነት ተመጣጣኝ ክፍያ የሚጠየቅባት አገር ነች፡፡ እንደ ህንድ ሁሉ ታይላንድም ተመጣጣኝ በሆነ ክፍያ ህክምና የሚገኝባት የሜዲካል ቱሪዝም
መዳረሻ አገር መሆኗ ይታወቃል፡፡ በተለይ ከውበት ጋር ለተያያዙ ቀዶ ጥገናዎችና ለአዕምሮ
ህክምናዎች ታይላንድ ተመራጭ አገር መሆኗን የጤና ድርጅቱ መረጃ ያመለክታል፡፡ የተለያዩ አገራት
ባለስልጣናትና ታዋቂ ግለሰቦች ህክምና ፍለጋ የሚጓዙባት ታይላንድ፤ አለምአቀፍ እውቅና ያላቸውና
ደረጃቸውን የጠበቁ ሆስፒታሎችም አሏት፡፡ ደቡብ አፍሪካም በውበት ቀዶ ጥገና ህክምናዋ የምትታወቅና በበርካታ አሜሪካውያንና አውሮፓውያን የምትጐበኝ የሜዲካል ቱሪዝም መዳረሻ አገር ነች፡፡ የጡት ማሳነስ፣ ማስተለቅ፣ የከንፈርና የአፍንጫ ማስተካከል፣ የውፍረት መጨመርና መቀነስ ህክምናዎች በደቡብ አፍሪካ በስፋት ይሰጣሉ፡፡ አገሪቱን ለሜዲካል ቱሪዝም መዳረሻነት ተመራጭ ያደረጓት የሚሰጡት የህክምና ዓይነቶች ብቻ ሳይሆኑ የህክምና ክፍያው ተመጣጣኝነትም ጭምር ነው፡፡ እነዚህ የውበት ማስተካከያ ህክምናዎች ከአውሮፓና ከአሜሪካ ዋጋቸው በግማሽ ይቀንሳል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ጥናት ያደረገውንና በአሜሪካ የሚገኘውን የደልዌር ዩንቨርሲቲ ጥናት ጠቅሶ የአለም ጤና ድርጅት መረጃ እንዳመለከተው፤ ለተለያዩ የጤና እክሎችና ለውበት የሚደረጉ ህክምናዎችን በህንድ፣ በታይላንድና በደቡብ አፍሪካ ማካሄድ በአውሮፓና በአሜሪካ የሚደረገው ህክምና ከሚጠይቀው ወጪ ከግማሽ በታች ይጠይቃል፡፡
 ህሙማኑ በእነዚህ አገራት ለሚያደርጉት ህክምና የሚከፍሉት ገንዘብ፣ የሆቴልና የመዝናኛ ወጪዎቻቸውንም የሚያካትት መሆኑ ደግሞ የበለጠ ተመራጭ ያደርጋቸዋል፡፡ የሜዲካል ቱሪዝም መዳረሻ በሆኑ አገራት ውስጥ የሚገኙት ሆስፒታሎች በአለም አቀፍ የጥራት ቁጥጥር ተቋማት እየተመዘኑ እውቅና የሚሰጣቸው ሲሆን በተለያዩ የአውሮፓና የአሜሪካ አገራት ውስጥ የሚሰጠውን የስፔሻላይዜሽን ትምህርት በተከታተሉ የህክምና ባለሙያዎች የተደራጁም ናቸው፡፡ እንደ አሜሪካ፣ እንግሊዝ፣ ጣሊያንና ፈረንሳይ ያሉ አገራት ውስጥ የሚገኙ ህሙማን ምንም እንኳን ሕክምናው በአገራቸው ቢገኝም በአነስተኛ ዋጋ ለመታከምና አገር ለማየት ሜዲካል ቱሪስት መሆኑን ይመርጣሉ፡፡ በዚህ ሳቢያም የሜዲካል ቱሪዝም ዘርፍ እጅግ እየሰፋና ለየአገራቱም ከፍተኛ የገቢ ምንጭ እየሆነ መጥቷል፡፡     



Published in ዋናው ጤና

    በሚዩንግ ሰንግ አጠቃላይ ሆስፒታል (ኮሪያ ሆስፒታል) የመድኀኒትና የህክምና መሳሪያዎች ክምችትና አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ሰሞኑን ድንገተኛ ፍተሻ የተካሄደ ሲሆን ከፍተሻው ጋር በተገናኘ ሆስፒታሉ ማብራሪያ እንዲሰጥ መጠየቁን ምንጮቻችን ገለፁ፡፡
ከምንጮቻችን ባገኘነው መረጃ መሠረት፤ የፌደራል የምግብ፣ የመድኃኒት የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን ባለፈው አርብ ድንገተኛ ፍተሻ በማድረግ በሆስፒታሉ ውስጥ የሚገኘውን የመድኃኒት ማከማቻ ክፍል ፣ የማደንዘዣ መድኃኒቶች ማስቀመጫ ክፍሎች፣ የህክምና መሳሪያዎችና ስቴራላይዝ ማድረጊያ ሥፍራዎችን አሽጎ ነበር፡፡ ባለፈው ሰኞ የባለሥልጣኑ ባለሙያዎች እሽጉን በመክፈት ምርመራቸውን ያከናወኑ ሲሆን በወቅቱ ስለተገኙ ነገሮች ፣ ስለ አሠራር ሒደቱ፣ እንዲሁምየ ሰራተኞችን የሙያ ብቃትና ፍቃድ የተመለከቱ መረጃዎች ሆስፒታሉ እንዲያቀርብ ደብዳቤ ተፅፎለታል፡፡በሆስፒታሉ በተደረገው ድንገተኛ ፍተሻ የተገኙት መድኃኒቶችና የህክምና መሳሪያዎች፤ በባለስልጣኑ እውቅናና ፈቃድ የሌላቸውና በባለስልጣኑ በኩል ተመርምረው ወደ አገር ውስጥ እንዲገቡ ፍቃድ ያልተሰጣቸው ናቸው ተብሏል፡፡
እነዚሁ መድኃኒቶችና ልዩ ልዩ የህክምና መገልገያ ቁሳቁሶችም በባለስልጣኑ የምርመራ ሰራተኞች የተወሰዱ ሲሆን፤ ሆስፒታሉ ስለእነዚህ ነገሮች በቂ ማብራሪያ እንዲሰጥ ተጠይቋል፡፡ ስለጉዳዩ ዝርዝር መረጃ ለማግኘት የፌደራል የምግብ የመድኃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን የሥራ ኃላፊዎችን ብንጠይቅም ጉዳዩ ገና በምርመራ ሂደት ላይ በመሆኑ መረጃ ለመስጠት እንደማይቻል ገልፀው የምርመራ ሂደቱን በተመለከተ ሪፖርት እየተዘጋጀ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡
አዲስ አድማስ ጋዜጣ ከዚህ ቀደምም በሆስፒታሉ አገልግሎት አሰጣጥ፣ በሰራተኞች አያያዝና በመድኃኒቶች አቅርቦት ዙሪያ የሚሰሙ ቅሬታና ችግሮችን የተመለከተ ዘገባ ማቅረቡ ይታወሳል፡፡

Published in ዜና

1. [የባራክ ኦባማ ጉብኝት፤ የትሪሊዮን ዶላሮች ጉባኤ፤ የ100% ምርጫ፤ ዘግናኞቹ ግድያዎች]
2. [የኤክስፖርት ድንዛዜ፣ “እድሜ ለዳያስፖራ”፣ የነዳጅ ዋጋ እና የሚኒስቴሩ አስገራሚ መግለጫ]

    በፖለቲካው መስክ፣ የባራክ ኦባማ ጉብኝትና የዩኤን የፋይናንስ ጉባኤ በበጎነት የሚጠቀሱ ክስተቶች ናቸው። በእርግጥ፣ የኦባማ የፖለቲካ ቅኝት፣ የአሜሪካ የነፃነትና የብልፅግና አርአያነትን ይወክላል ብዬ አላስብም።
እንደ ኢትዮጵያ የመሳሰሉ አገራት፣ ወደ ተሻለ አቅጣጫ እንዲጓዙ፣ የመገፋፋት ብቃት አላቸው ብዬም አላምንም።
ቢሆንም ግን፣ የኦባማ ጉብኝት፣ ለኢትዮጵያ መልካም ክስተት ነው። ከአሜሪካ የተሻለ የስልጣኔ አርአያ ስለሌለ፣ ከአሜሪካ ጋር መወዳጀት ጥሩ ነው። የኢትዮጵያ ፖለቲካና ኢኮኖሚ በተወሰነ ደረጃ እንዲሻሻል፣ ያም ባይሆን፣ ይብስ እንዳይበላሽ ይረዳ ይሆናል - የአሜሪካ ወዳጅነት። በዚያ ላይ፣ የስራ እድል የሚከፍቱ፣ የቢዝነስ አሰራርን ለማሻሻል የሚያግዙ የውጭ ኢንቨስተሮች፣ ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጡም ያደፋፍር ይሆናል።
የዩኤን ጉባኤስ? ለድሃ አገራት የገንዘብ ምንጭ ለማፈላለግ፣ በአዲስ አበባ የተካሄደው የዩኤን የፋይናንስ ጉባኤ፣ እንደ ድሮው ከቢሊዮን ዶላሮች አልፎ፣ ስለ ትሪሊዮን ዶላሮች የተወራበት ጉባኤ ነው። ግን፣ ጉባኤው ለኢትዮጵያ እንደ በጎ አጋጣሚ የሚቆጠረው፣ ዩኤን እንደሚያወራው፣ ዶላር ይጎርፍልናል በሚል አይደለም።
እንደ ካሁን ቀደሙ፣ አብዛኛው የእርዳታ ወሬ፣ በዚያው ወሬ ሆኖ ነው የሚቀረው።  የተወሰነ እርዳታ አይመጣም ማለት አይደለም። ይመጣል። ነገር ግን፣ እርዳታ... ካሁን በፊት እንደታየው፣ ለተወሰነ ጊዜ በሕይወት ለመቆየትና ከአደጋ ለማምለጥ ያግዛል እንጂ፣ ብልፅግናን አያስገኝም።
ቢሆንም፣ ስብሰባው በአዲስ አበባ መካሄዱ መልካም ነው። በሺ የሚቆጠሩ ተሰብሳቢዎች የተገኙበት ትልቅ ጉባኤ መሆኑ፣ አንድ ነገር ነው። ግን፣ ከዚህም ይበልጣል። እንደ ሌላው ጊዜ፣ በአንድ አዳራሽ የተካሄደ ወይም በጥቂት ስብሰባዎች የተጠናቀቀ ጉባኤ አይደለም። ጎን ለጎን፣ ከ200 በላይ ስብሰባዎች ናቸው የተካሄዱት። ትልልቆቹ ሆቴሎች፣ በአንድ ቀን ውስጥ፣ ከአምስት እስከ ሰባት አዳራሾችን፣ ማከራየት ሲችሉ አስቡት። አንዱን አዳራሽ ሁለቴና ሦስቴ ሲያከራዩስ? ጉባኤው፣ ለበርካታ ሆቴሎች፣ የአመቱ ትልቅ ባለውለታ ነው።
የ100% ምርጫ
ሌላኛው የአመቱ ክስተት፣ ፉክክር የራቀውና 100% ኢህአዴግ ያሸነፈበት የፓርላማ ምርጫ ነው። የአገራችን ፖለቲካ፣ ገና ኋላቀር መሆኑን የሚመሰክር ምርጫ ቢሆንም፣ አወንታዊ ነገር እናውጣለት ብለን መሞከር እንችላለን።
አንደኛ ነገር፣ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን፣ የፓርቲዎችን ክርክር በቴሌቪዥን አይተናል። ሁለተኛ ነገር፣ ምርጫው ላይ፣ አንዳችም የፉክክር ምልክት አልነበረም ማለት አይደለም። ተቃዋሚ ፓርቲዎች የፓርላማ ወንበር ባያሸንፉም፣ በበርካታ ከተሞች፣ እስከ 30 በመቶ ድረስ ድምፅ ያገኙበት ምርጫ እንደነበረ ማስታወስ ያስፈልጋል። ሦስተኛ ነገር፣ አላስፈላጊ ቀውስ አልተፈጠረም።
ከዚህ ውጭ፣ ያው፣ ወደፊት እንዲሻሻልና፣ ከፉክክር ጋር በሰላም የሚካሄድ ምርጫ እውን እንዲሆን መመኘትና መጣር ነው።

ሃዘንና ቁጭት - በአክራሪነትና በዘረኝነት
2007 ዓ.ም፣ በጣም አሳዛኝ ክስተቶችን ያስተናገድንበት  አመት ነው። አለምን እያናወጠ የሚገኘው የሃይማኖት አክራሪነትና አሸባሪነት፣ ኢትዮጵያዊያንን የሚምር አልሆነም። በእርግጥም፣ ከየትኛውም እምነት ቢሆን፣ ከእስልምናም ሆነ ከክርስትና፣ ከሂንዱም ከሆነ ከቡድሃ እምነት፣ ብዙም ልዩነት የለውም። የሃይማኖት አክራሪነት፣ ማንንም አይምርም። ይሄ እውነት ነው። እንዲያም ሆኖ፣ አሸባሪዎች፤ ሊቢያ ውስጥ፣ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ላይ የፈፀሙት አረመኔያዊ ግድያ፣... አእምሮ ከሌለው ክፉ አውሬ እንኳ የማይጠበቅ ነው።
ያልታጠቁ ሲቪሎችን፣ ለዚያውም ስደተኞችን በጅምላ መጨፍጨፍ ምን ይባላል?... የሃይማኖት አክራሪነት የእብደት መጠን፣ “እዚህ ወይም እዚያ ድረስ ነው” ተብሎ የሚገለፅ አልሆነም።
በዚህ መሃል፣ ገዢው ፓርቲ፣ ያንንም ያንንም “አሸባሪ” ብሎ እየወነጀለ፣ እጅግ አሳሳቢ የሆነውን ጉዳይ፣ ተራ የፖለቲካ መጫወቻ ካርድ ሲያደርገው ማየት ያሳዝናል። እጅግ አላዋቂነት ነው። ይህም ብቻ አይደለም።  
ሁሉም ባይሆኑም፣ በርካታ ተቃዋሚዎችም፣ ‘ገዢውን ፓርቲ ለማሳጣት ይጠቅመናል’ በሚል ቀሽም ስሌት፣ ጨርሶ የሃይማኖት አክራሪነትና የሽብር ስጋት የሌለ እስከማስመሰል ይደርሳሉ።
እባካችሁ፣ ገዢው ፓርቲ እና ተቃዋሚዎች፣ ... ምናለ፣ አንዳንድ ከባባድ ጉዳዮች፣ በጭራሽ የፖለቲካ መጫወቻ ካርድ መሆን እንደሌለባቸው ብትገነዘቡልን።
የዘረኝነት እብደትም፣ እዚህ ላይ መጥቀስ ያስፈልጋል። የዘረኝነት እብደት፣ ገደብ እንደሌለው፣ በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እና ሌሎች ስደተኞች ላይ በተፈፀመው ዘግናኝ ግድያ አይተናል።
ድሮ ድሮ የምናውቀው፣ በዘር የተቧደኑ ጥቂት ነጮች፣ በጥቁሮች ላይ ጥቃት ሲፈፅሙ፤... ወይም ሮበርት ሙጋቤ እንዳደረጉት፣ በዘር የተቧደኑ ጥቂት ጥቁሮች፣ በነጮች ላይ ሲዘምቱ ነበር። ሮበርት ሙጋቤን የሚያደንቁ ‘አላዋቂዎች’፣ ምንን እያደነቁ እንደሆነ መች አወቁ?
ዘረኝነት፣ “ጥቁርና ነጭ” በሚል መቧደኛ ውስጥ ታጥሮ፣ እዚያው እንደተቀመጠ ሊቀር አይችልም። በአገር፣ በብሄረሰብ፣ በጎሳ፣ በወረዳ... እያለ፣ ከላይ እስከ ታች ሁሉንም ሳያዳርስ፣ የጥፋት ሰደዱ አይቆምም - ሙሉ ለሙሉ ካላስወገዱት በቀር። በተግባር እያየነው አይደል?

በኢኮኖሚው መስክ፡
“የነዳጅ ዋጋና አስገራሚው የንግድ ሚኒስቴር ስጋት”
(“የኤክስፖርት ድንዛዜ” ፣ “እድሜ ለዳያስፖራ”፣ “አስፊሪ የብድር ክምር”)
በ2007፣ ለኢትዮጵያ ትልቅ ትርጉም ያለው አለማቀፍ የኢኮኖሚ ዜና፣ የነዳጅ ዋጋ መቀነሱ ነው። ባለፉት ስድስት ወራት፣ የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ፣ በትንሹ ከፍና ዝቅ ቢልም፣ ከአመት በፊት ከነበረው ዋጋ ጋር ሲነፃፀር ግን፣ በጣም ወርዷል -  በበርሜል ከ110 ዶላር ወደ 50 ምናምን ዶላር። ይህም ብቻ አይደለም።
የነዳጅ ዋጋ፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ፣ እንደገና ሊጨምር ይችላል ተብሎ አይገመትም። አንደኛ ነገር፣ የበርካታ አገራት ኢኮኖሚ፣ ብዙ የመነቃቃት አዝማሚያ አይታይበትም። በርካታዎቹ ደግሞ፣ የለየለት ቀውስ ውስጥ ገብተዋል። ሁለተኛ ነገር፣ የሳዑዲ አረቢያ መንግስትና ሌሎቹ፣ የነዳጅ ምርት ለመቀነስ ፍላጎት እንደሌላቸው በተደጋጋሚ ገልፀዋል። እንዲያውም፣ የነዳጅ ምርት ጨምሯል - በተለይ አሜሪካ ውስጥ በተስፋፋውና ‘ፍራኪንግ’ የተሰኘ አዲስ የቴክኖሎጂ ፈጠራ አማካኝነት።
ሦስተኛ ነገር፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ፣ የቻይና ኢኮኖሚ፣ በበርካታ ችግሮች ሳቢያ መደነቃቀፍ አብዝቷል። የኢኮኖሚ እክል ሲያጋጥም፣ የነዳጅ ፍጆታ እንደሚቀንስ ሲያስረዱ የከረሙት አለማቀፍ የሚዲያ ተቋማት፤ ባለፉት ጥቂት ሳምንታት፣ ከቻይና የኢኮኖሚ እክል ጋር፣ የነዳጅ ዋጋ ይበልጥ እንደወረደ ዘግበዋል። ለሚቀጥሉት በርካታ ወራት፣ ያን ያህልም የዋጋ ጭማሪ አይከሰትም ሲሉም ግምታቸውን ገልፀዋል። ይሄ፣ ለኢትዮጵያ መልካም የኢኮኖሚ ዜና ነው። መንግስት የተጣራ ነዳጅ ለማስመጣት የሚከፍለው ዋጋ በ45% እንደቀነሰ፣ በቅርቡ ብሔራዊ ባንክ ባወጣው ሪፖርት ገልፆ የለ! ግን ምን ማለት ነው? ልዩነቱን መመልከት ትችላላችሁ።
በ2007 ዓ.ም ከጥር እስከ መጋቢት መጨረሻ፣ የተጣራ ነዳጅ ገዝቶ ወደ ኢትዮጵያ ለማስመጣት የዋለው ገንዘብ፣ 317 ሚሊዮን ዶላር ነው።
በ2006 ዓ.ም የነበረው ዋጋ ባይቀንስ ኖሮ ግን፣ 583 ሚሊዮን ዶላር ያስፈልግ ነበር። ልዩነቱ ቀላል አይደለም። በሦስት ወራት ብቻ፣ 266 ሚሊዮን ዶላር ማዳን፣ እጅግ ትልቅ ነገር ነው። የነዳጅ ዋጋ፣ በዚህ ከቀጠለ፣ በዓመት ውስጥ፣ ከአንድ ቢሊዮን ዶላር በላይ ወጪ ዳነ ማለት ነው - ወደ 22 ቢሊዮን ብር ገደማ።
“ጥሩ ነው። ጥሩ ነው። ግን፣ ጥሩነቱ አየር ላይ እንደተንሳፈፈ ቀረሳ” የሚል ስሜት ቢፈጠርባችሁ አይገርምም። ትንሽ ወደ መሬት እናውርደው።  
አምና፤ በመጋቢት 2006 ዓ.ም፣ ቤንዚን ገዝቶ ወደ አገር ለማስገባት፣ በሊትር 14.70 ብር ይፈጅ ነበር።
ከወደብ ለመረከብና ወደ ነዳጅ ማደያዎች ለማድረስ፣ የማጓጓዣ ወጪ አለ። የታክስ ክፍያም ይጨመርበታል። የችርቻሮ የአገልግሎት ክፍያና ሌሎችም ወዘተ...። ነገር ግን፣ የችርቻሮ ዋጋው፣ በገበያ ውድድር ሳይሆን፣ መንግስት በሚያወጣው ተመን ነው የሚወሰነው። እናም በሊትር፣ 20.30 ብር ነበር የሚቸረቸረው - አምና በመጋቢት ወር።
[በ14.70 ተገዝቶ ይመጣል። በ20.30 ይቸረቸራል]
ዘንድሮስ?
ዋጋው ስለወረደ፣ ቤንዚን ወደ አገር ለማስገባት፣ ወጪው ከ8.50 ብር በታች ሆኗል - ለአንድ ሊትር ቤንዚን።
መንግስት የተመነለት የችርቻሮ ዋጋስ? ለአንድ ሊትር፣ 17.90 ብር ነው።
[በ8.50 ተገዝቶ ይመጣል። በ17.90 ይቸረቸራል]። ይሄ በፍፁም ተገቢ ያልሆነ ዋጋ ነው የምትሉ ከሆነ አልተሳሳችሁም።
የአለም ባንክ፣ ባለፈው ሐምሌ ባወጣው ሪፖርት፣ የችርቻሮ ዋጋው፣ ወደ 14.80 ብር መውረድ እንደነበረበት ይጠቁማል። (4TH ETHIOPIA ECONOMIC UPDATE - ገፅ 15)። ግን፣ አልወረደም። በዚህ ምክንያት ብቻ ከቤንዚንና ከነናፍጣ፣ መንግስት የሚያገኘው ትርፍ፣ ከ7.5 ቢሊዮን ብር በላይ ነው። ‘ያልታሰበ ሲሳይ’ ሆኖ ሊታየው ይችላል።
በዚህ መሃል፣ ረቡዕ እለት፣ የንግድ ሚኒስቴር ያወጣውን መግለጫ ሰምታችሁ ይሆናል። በአለም ገበያ፣ የነዳጅ ዋጋ ይበልጥ መውረዱን ይጠቅሳል መግለጫው። የአገር ውስጥ የችርቻሮ ዋጋ ግን አይቀየርም፡፡ እስካሁን የነበረው ተመን፣ በመስከረም ወርም እንዲቀጥል ወስኛለሁ ብሏል ሚኒስቴሩ።
የችርቻሮ ዋጋው፣ ከአለም ገበያ ጋር እንዲቀንስ የማይደረገው ለምንድነው? ሚኒስቴሩ፣ ለዚህ ጥያቄ ምላሽ አዘጋጅቷል።
የእስካሁኑ የዋጋ ተመን እንዲቀጥል የተወሰነው፣ የአገሪቱ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች በተረጋጋ ሁኔታ እንዲቀጥሉ በማሰብ እንደሆነ ሚኒስቴሩ ገልጿል።
እንዴት እንዴት?
የአለም ገበያን ተከትሎ፣ የችርቻሮ ዋጋው ከተቀነሰ፣ “የአገሪቱ ኢኮኖሚና ማህበራዊ እንቅስቃሴ ይናጋል” ማለት ነው? የንግድ ሚኒስቴር ስጋት፣ ግራ የሚያጋባ ነው። “በአለም ታይቶና ተሰምቶ የማይታወቅ አስገራሚ ስጋት” ተብሎ ለድንቃድንቅ መዝገብ ቢመረጥ አይበዛበትም።
“አንተ፣ ዋጋውን አስተካክል እንጂ፣ ቀሪውን ለኛ ተወው። ጨርሶ ስጋት አይግባህ” ብላችሁ ልታሳምኑት ከቻላችሁ ሞክሩ - የሚሰማ ከሆነ።
እንደሚመስለኝ ግን፣ መንግስት ይህንን የገንዘብ ምንጭ በቀላሉ ለመልቀቅ ፈቃደኛ ይሆናል ብዬ አልጠብቅም። መዓት ወጪዎችን ለመሸፈን ገንዘብ ያስፈልገዋል። እየተከመሩ የመጡ እዳዎችን ለመክፈል፣ ገንዘብ ያስፈልገዋል። አስቀድሞ፣ ወጪዎችን ለመቀነስና ብድር ላለማብዛት የማይጠነቀቅ ከሆነ፣ ምን ማድረግ ይቻላል?
ለማንኛውም ግን፣ በአለም ገበያ፣ የነዳጅ ዋጋ መቀነሱ ጥሩ ነው። አንድ ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሪ ከየት ይመጣ ነበር?
ከኤክስፖርት?
የኤክስፖርት ነገርማ፣ አሳዛኝ ሆኗል። ላለፉት አራት አመታት፣ ምንም አይነት እድገት ሳይታይበት፣ እዚያው በነበረበት ቦታ እየረገጠ ነው። የጠቅላይ ሚኒስትር አማካሪ፣ ዶ/ር አርከበ እቁባይ የተናገሩትን መጥቀስ ይበቃል - “በጣም በጣም አሳሳቢ ነው” ብለዋል፡፡  
እንደ መንግስት ‘እቅድ’ ቢሆን ኖሮ፣ ወደ ውጭ ምርታቸውን የሚልኩ ድርጅቶች እየበዙና እያደጉ፣ በአመት የሚያገኙት የሽያጭ ገቢ፣ ዘንድሮ ቢያንስ ቢያንስ ስምንት ቢሊዮን ዶላር ይደርስ ነበር። ግን አልሆነም። ከአራት አመት በፊት የነበረበት ቦታ ላይ ቆሟል - 3 ቢሊዮን ዶላር ላይ።
ሌላኛው፣ የውጭ ምንዛሪ ምንጭ፣ የውጭ እርዳታና ብድር ነው። እርዳታው ባይቋረጥም፣ እንደታሰበው አልጨመረም። እርዳታ ሰጪዎቹ የአውሮፓና የአሜሪካ መንግስታት፣ ተጨማሪ እርዳታ የመስጠት አቅማቸው ተንጠፍጥፏል። እነሱ ራሳቸው፣ በኢኮኖሚ ድንዛዜና በበጀት እጥረት ተወጥረዋል። ብድርስ? ብድርስ አልጠፋም። ግን፣ ምን ዋጋ አለው? ብድር ሲደራረብ ያስፈራል። እንዴት ተደርጎ ከነወለዱ መመለስ እንደሚቻል እንጃ!
ምንም፣ መልካም ወሬ የለም ማለት ግን አይደለም። “እድሜ ለዳያስፖራ” ብንል ይሻላል። ለቤተሰብ የሚልኩት ገንዘብ፣ ከአመት አመት እየጨመረ መጥቷል። በ2007 ዓ.ም የመጀመሪያዎቹ ስድስት ወራት ብቻ፣ ከዳያስፖራ የመጣው ገንዘብ፣ ከ1.7 ቢሊዮን ዶላር በላይ ነው። በአመት፣ ወደ 3.5 ቢሊዮን ዶላር ይጠጋል። ከኤክፖርት ገቢ ይበልጣል ማለት ነው።
በጥቅሉ ሲታይ፣ በ2007 ዓ.ም፣ አገሪቱ በውጭ ምንዛሪ እጥረት፣ ጉድ ከመሆን የተረፈችው፣ በሁለት ምክንያቶች ነው ማለት ይቻላል - ‘ዳያስፖራዎች’ ለቤተሰብ የሚልኩት ገንዘብ በመጨመሩና በአለም ገበያ የነዳጅ ዋጋ በመቀነሱ።

አንድ አንበሳ እያረጀ መጣ፡፡ ከሰፈር ወጥቶ ወደ ሌላ ጫካ መሄድ አቃተው፡፡ ልጆቹም ሆኑ ሚስቱ ብዙ ትኩረት የሚሰጡት ዓይነት አልሆኑም፡፡ ሲያረጁ አይበጁ እንዲሉ ሆኗል፡፡
ከዕለት ዕለት እየዛለ፣ እንደ ልብ መራመድም እያቃተው ሄደ፡፡
አንድ ቀን ልጆቹን ጠርቶ፤
“ልጆቼ! እኔ እናንተን ለማሳደግ በየጫካው ተንከራትቻለሁ፡፡ አድኜ መግቤያችኋለሁ! አደንም አስተምሬያችኋለሁ! መከበሪያችሁም ሆኛለሁ! ዛሬ ግን ሁላችሁም በእኔ ላይ ፊታችሁን አዞራችሁብኝ!”
“ኧረ ፊታችንን አላዞርንብህም አባባ! አንተ አርጅተህ ቤት ስትውል፤ ተሯሩጠን አድነን፣ ቤታችን ሞቅ እንዳለ እንዲቀጥል እየጣርን ነው፡፡ እንግዲህ አንተም ውጪ ውጪ ማለትህን ትተህ፣ ሰብሰብ ብለህ ተቀመጥ፡፡ መሞቻህ ከደረሰም እኛ ተንከባክበን እንቀብርሃለን!” አሉት ልጆቹ፤ እየተፈራረቁ፡፡
“አይ ልጆቼ! እንኳን ሞት እርጅና አለ አይደለም ወይ?!”
“ለምን እንዲህ አልክ አባባ?” አለ አንደኛው ልጅ፡፡
“እርጅና በቁም መረሳት ነው ልጄ”
“እንዴት አባባ?” አለ ሌላኛው ልጅ፡፡
“ይሄው እናንተ የምታደርጉት ማስረጃ ነው! ጀማው ህብረተ-እንስሳን ተመልከቱ - ዞር ብሎ የሚያየኝ ጠፋ! ንጉሳቸው እንደነበርኩ የሚያስታውስ፣ ውለታዬን ከቁም ነገር የሚቆጥር አንድ እንስሳ ጠፋ! ግን ልጆቼ፤ ሁሌ ልጅ ሆኖ አይኖርም - ሁላችሁም አንድ በአንድ ተራችሁን እያረጃችሁ ትሄዳላችሁ፤ ትረሳላችሁ፣ ትጣላላችሁ!”  አለ፡፡
“አሁን ምን እናድርግልህ አባባ?”
“አሁንማ እርስ በርሳችሁ ሳትከፋፈሉ፣ ሳትሻሙ፣ ሳትጣሉ፤ ተመካከሩ፡፡ እኔንም ሆነ በእኔ ዕድሜ ያሉትን ሁሉ አትናቁ፣ አትኮንኑ! የወደፊቱን ብታስቡ ከብዙ መዘዝ ትወጣላችሁ! አለበለዚያ ያለጊዜ ማርጀትም ይመጣል! ያ ደግሞ ከእርጅና የከፋ እርግማን፣ ከመርገምት ሁሉ የከፋ መርገምት ነው! የጋራ ጫካችንን እንዴት እናቆየው ብላችሁ ጨክናችሁና በቅንነት ካልተነጋገራችሁ ጫካውም ጫካ አይሆን፣ ቤታችሁም ቤት አይሆንም!”
“ታዲያ ምን ታወርሰናለህ?”
“እስካሁን የነገርኳችሁን ምክርና የእኔን የልጅነት ልብ!! ለማንኛውም ያለፈውን አትኮንኑ፣ እርስ በርስ አትካሰሱ! ከሁሉም በላይ ግን ዳኛ አያሳጣችሁ!” ብሎ አሸለበ፡፡
*           *         *
እርስ በርስ አለመተሳሰብ፣ አለመነጋገር፣ ነገር በሆድ መያዝ ክፉ ልማድ ነው፡፡ አባትህን መዘንጋት ደግ አይደለም፡፡ በውርስ መልክ መናቆርን መረከብ መርገምት ነው፡፡ “አያረጅ የለም አይለዋወጥ” የሚለውን ሁሌም ልብ ማለት ነው፡፡ በአንፃሩ አዲሱ መምጣቱ አይቀሬ ነው” (The New is Invincible) የሚለውንም ማጤን ነው! ሁሉ ነገር ተለዋዋጭ ነው፡፡ አሮጌው ያልፋል፤ አዲሱ ይተካል፡፡ ከአሮጌው አዲሱ ልብ ውስጥ የሚቀር ነገር አለ፡፡
የሩሲያን፣ የቻይናንና የኩባን መሪዎች አስመልክቶ ስብሀት ገ/እግዚአብሔር “ሽፍቶችና መሪዎች” በሚለው ጽሑፉ፤ “ባጠቃላይ እንዲያው በጭፍን ያህል ስንናገር፣ በአንድ ልብ፣ በአንድ ወኔ፣ ለአንድ ዓላማ ሲዋጉ የነበሩት ሽፍቶች፣ መሪዎች በሆኑ በማግሥቱ፤ ዓላማቸውም ልባቸውም መለያየት ይጀምራል፡፡ ልዩነቶቻቸው እየበዙ እየከረሩ ሲሄዱ፣ ጠላትነት እየተንፏቀቀ መኻላቸው ይገባል፡፡ በራሺያ ስታሊን ትሮስኪን ያባርረዋል፡፡ ከዚያም ሜክሲኮ ድረስ ልኮ ያስገድለዋል፡፡ ሽፍቶች የነበሩት የትሮትስኪ ወገኖች፣ ሽፍቶች በነበሩት የስታሊን ወገኖች ይጨፈጨፋሉ፡፡ በቻይና ሽፍታ የነበረው ሊዩ-ሻዎ-ቺ ሽፍቶቹ ወደ መሪዎቹ ሲለወጡ የመከላከያ ሚኒስትር ሆኖ ቆየ - ያውም አሪፍ! ማኢና ሊዮ የኋላ ኋላ ተቃቃሩ … አንድ ቀን ሊዮ - ሻዎ - ቺ ከአገር ለመጥፋት በአውሮፕላን ሲበር፣ የሊቀመንበር ማኦ ወገኖች ነቅተውበት ኖሮ ተኩሰው አውሮፕላኑን አጋይተው ይገሉታል፡፡
ወደ ኩባ ስንመጣ ግን ቼ እና ካስትሮ እንደተባበሩ እንደተዋደዱ ተለያዩ፡፡ ትምህርታችንን ከገለጠልን ጋሽ ስብሃት ትልቅ ትምህርት ጥሎልን አልፏል፡፡ ሥልጣን እንዳያለያየንና ዓላማችንን እንዳንረሳ! ያም ሆኖ ለስልጣን ያበቃናቸው ሰዎች፤ ስልጣናቸው ላይ እንዳይተኙ መጠንቀቅ ያባት ነው፡፡ አስረጅ ይሆነን ዘንድ የደጃች ማሩ ወግ እነሆ፡-
“ደጃች ማሩ አሽከሮቻቸውን ሰብስበው አንዱን ፊታውራሪ፣ አንዱን ግራዝማች፣ ወዘተ ብለው ሾሙ አሉ፡፡ ሆኖም ምንም ሥራ የለም፡፡ ስለዚህ አሽከሮች ጋቢ ለብሰው በየጠዋቱ ፀሐይ ይሞቃሉ፡፡
መንገደኛ አይቷቸው፤ “ምን እየሰራችሁ ነው?” ይላቸዋል፡፡
ተሿሚዎቹም፤ “ዝም ብለህ እለፍ! የደጃች ማሩ እሥረኞች ነን!” አሉት፡፡ ከዚህ ይሰውረን!!
ቅርንጫፍ ባበዛን ቁጥር የሚመች ሁኔታ አይኖርም፡፡ ለሰዓቱ ይኮናል? ስንቱን ማርካት ይቻላል?  ተመቸኝ ብሎ የማይፏልሉበት፣ አልተመቸኝም ብሎ እሪዬ - ወዬ የሚሉበት ሁኔታ እንዳይፈጠር ትልቅ ዐይን ያስፈልጋል! በአንፃሩ ዕውነተኛ ተተኪ፣ ዕውነተኛ ወራሽ አለማግኘት መረገም ነው፡፡ “ከሁለት የወለደ አይደሰት፤ ሳይወልድ የሞተ አስተዛዛኝ የለው!” የሚለው ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ሃቅ ነው!!

Published in ርዕሰ አንቀፅ
Page 15 of 16