Saturday, 20 September 2014 11:50

“ስውር ስፌት ቁ.2” ተመረቀ

በጋዜጠኛ፣ ገጣሚና ተርጓሚ ነቢይ መኰንን የተጻፈው “ስውር ስፌት ቁ.2” የግጥም መድብል ትናንት ምሽት
በዋቢ ሸበሌ ሆቴል አዳራሽ ተመረቀ፡፡የኪነጥበብ ቤተሰቦችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት
በተከናወነው የምረቃ ስነ ስርዓት ላይ፣ ገጣሚውን ጨምሮ አንጋፋና ወጣት ገጣሚያን ስራዎቻቸውን ለታዳሚው
አቅርበዋል፡፡
ገጣሚ ነቢይ በመኰንን ከዚህ በፊት “ጥቁር፣ ነጭ ግራጫ ግጥሞች” እና “ስውር ስፌት ቁ.1” የግጥም መፃህፍት
ለአንባቢ ያበረከተ ሲሆን፣ በታዋቂዋ አሜሪካዊት ደራሲ ማርጋሬት ሚሼል የተጻፈውን “Gone With The
Wind” የተሰኘ ተወዳጅ የረጅም ልቦለድ መጽሃፍ፣ “ነገም ሌላ ቀን ነው” በሚል ርዕስ ወደ አማርኛ ተርጉሞ
በማቅረብ ይታወቃል፡፡
“ስውር ስፌት ቁ.2” በመጽሃፍት መደብሮችና በአዟሪዎች እየተሸጠ ይገኛል፡፡

“መንገድ ተዘረጋ
መንገድ ተቀየሰ
በተራማጅ እጦት
መልሶ ፈረሰ!...”
በገጣሚ አክሊሉ ገብረ መድህን የተጻፈው “የጭቃ ጅራፎች” የተሰኘ የግጥም መጽሃፍ፣ ነገ ከምሽቱ 11፡30 ሰዓት
በዋቢ ሸበሌ ሆቴል አዳራሽ ይመረቃል፡፡
በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጠነጥኑ 50 የገጣሚው የግጥም ስራዎች የተካተቱበት መጽሃፉ 92 ገጾች
ያሉት ሲሆን በተለያዩ መጽሃፍት መደብሮችና አዟሪዎች ዘንድ በ20 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡
የጥበብ አፍቃሪዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በሚገኙበት የመጽሃፉ የምረቃ ስነ ስርዓት ላይ፣ አንጋፋና
ወጣት ገጣሚያን ስራዎቻቸውን ያቀርባሉ፡፡

“ነጻ አርት ቪሌጅ” በማካሄድ ላይ የሚገኘው ‘ነጻ ሃሳብ’ የተሰኘ የሥነ ጥበብ ፌስቲቫል አካል የሆነው የስዕል ትርዒት ዛሬ ከቀኑ 9 ሰዓት በ“ነጻ አርት ቪሌጅ” ይከፈታል፡፡ነጻ አርት ቪሌጅ ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ እንዳለው፣ ከዛሬ ጀምሮ ለተመልካች ክፍት በሚሆነው በዚህ የስዕል ትርኢት ላይ በ30 ሰዓሊያን የተሰሩ የሥነ ጥበብ ስራዎች ለእይታ ይቀርባሉ፡፡

ከኢትዮጵያ ቴሌኮም ይልቅ ህልሜን አመንኩት!

    ባለፈው ሳምንት በህልሜ ያየሁት ነገር አስገራሚ ነው፡፡ በአብዛኛው በህልማችን የምናየው ነገር የግል ህይወታችን ላይ የሚያተኩር ይመስለኛል፡፡ መቼም ናላውን ከሚያዞረው የኑሮ ውድነት ሃሳብ ወጥቶ ስለአገሩ ባለ ሁለት ዲጂት የኢኮኖሚ ዕድገት በህልሙ የሚያይ ሰው ያለ አይመስለኝም፡፡ (ቢያይማ ከኑሮ ውድነት ይወጣ ነበር!) ስለ አገሪቱ የዲሞክራሲያዊ ሥርዓት መጎልበት ወይም ስለ ስልጡን የፖለቲካ ባህል መዳበር ተኝቶ የሚያልም አለ ብዬ አልገምትም፡፡ (በህልም ዲሞክራሲ ማየት እንዴት ነው? ) በነገራችሁ ላይ ኢህአዴግ በህልሙ ያየውን ነገር ሁሉ እኛም ብናይለት (“ኮፒ ፔስት” ነው ታዲያ!) እንዴት ጮቤ እንደሚረግጥ አልነግራችሁም፡፡ በቃ ሃሳባችን ከሃሳቡ፣ህልማችን ከህልሙ ቢገጥምለት በእድሜው ላይ 40 ዓመት ይጨምር ነበር (ከ30-40 ዓመት በሥልጣን ላይ ለመቆየት ካሰበው ውጭ!) አንዳንዴ ሳስበው “እኔን ምሰሉ!” ማለት ምን ክፋት አለው እላለሁ፡፡

(በፍቅር ከሆነ የለውም!) ነገር የሚመጣው መቼ መሰላችሁ? በውዴታ ሳይሆን በግዴታ ምሰሉኝ ሲባል ነው፡፡ በተለይ ደግሞ ሰርክ አፉን “ዲሞክራሲ” በሚል ቃል ለሚያሟሽ ፓርቲ፤ በግድ “እኔን ሁኑ” ማለት ጨርሶ አያስኬድም፡፡ (ጸረ - ዲሞክራሲያዊ ነው!) ለነገሩ እኔን ምሰሉ እኮ ማለት ሌላ አይደለም - በአብዮታዊ ዲሞክራሲ ጠበል ተጠመቁ ማለት ነው፡፡ (የወደደ ይጠመቃል!) እኔ የምለው---ከአዲስ አበባ ህዝብ ውስጥ ምን ያህሉ “ልማታዊ”፣ ምን ያህሉ ደግሞ “ኪራይ ሰብሳቢ” እንደሆነ በጥናት የተደገፈ መረጃ አለ እንዴ? (ለጠቅላላ እውቀት ነው!) እንደ ኢህአዴግ ልፋት ቢሆንማ፣ ይሄኔ ከጠቅላላው የአገሪቱ ህዝብ 95.8 በመቶ ያህሉ “ልማታዊ” ይሆን ነበር፡፡ (ከምርጫ ውጤት ጋር ተመሳሰለባችሁ አይደል!?) አንድ ጥያቄ አለኝ -----ከኢህአዴግ ጋር ንኪኪ ሳይኖር (የፎረም… የሊግ.. ምናምን!) ልማታዊ መሆን ይቻል ይሆን? (ልማታዊ ባለሃብት፣ ልማታዊ ቲያትረኛ፣ ልማታዊ ዘፋኝ፣ ልማታዊ ሃኪም፣ ልማታዊ ጋዜጠኛ፣ ልማታዊ ሰው … ወዘተ!!) የ2007 እቅዴ በኢህአዴግ ያልታቀፈ ልማታዊ ጋዜጠኛ መሆን ነው፡፡ (“አብዮታዊ ዲሞክራሲ” አልወጣኝም!) አያችሁልኝ የኔን ነገር --- ስለ ኢህአዴግ ህልም ሳወራ የራሴን ህልም ሳልነግራችሁ! እናላችሁ --- ባለፈው ሳምንት በዓይነቱ ለየት ያለ፣ “ውጤት ተኮር” ህልም ነው ያየሁላችሁ፡፡

(በአፍሪካ በዓይነቱ የመጀመሪያው ህልም ሳይሆን አይቀርም!) አይዞአችሁ አትጨናነቁ ---የእኔ ህልም cost effective ነው - ቡናና ህልም ፈቺ አይፈልግም፡፡ ወደ ህልሜ ከመግባቴ በፊት አንዳንድ መረጃ ልጠቁማችሁ፡፡ እንግዲህ በቢሮአችን የስልክና የኢንተርኔት አገልግሎት ከተቋረጠ ወደ ሁለት ወር ገደማ ሆኖታል፡፡ የኢትዮ ቴሌኮም ሃላፊ በቴሌቪዥን መስኮት ቀርበው፣ “ከእንግዲህ የኢንተርኔትና የኔትዎርክ ችግር አከተመ” ባሉ በሳምንቱ ሁለቱንም አጣን፡፡ ከዚያስ? ከሁለት ወር ገደማ በኋላ ባለፈው እሁድ፣ የተቋረጠው የቢሮአችን ኢንተርኔት በህልሜ ሲሰራ አየሁ፡፡ በህልሜ ነው ያልኩት፡፡ ህልሜ ግን ከሌሎች ህልሞች ለየት ያለ ነበር፡፡ በነጋታው ቢሮ ስገባ ህልሜ እውን ሆኗል፡፡ ኢንተርኔታችን መስራት ጀምሯል!! በህልሜ ያሁትን ኢንተርኔት፣ በነጋታው በእውኔ አየሁት፡ እናም ከአሁን በኋላ የኔትዎርክና የኢንተርኔትን ጉዳይ በተመለከተ፣ ኢትዮ-ቴሌኮምን ሳይሆን ህልሜን ነው የማምነው! ይታያችሁ… ላለፉት 2 ወራት ከቴሌ አካባቢ ዝር ያለ ሰው የለም፤ በዚህ ጊዜ መስራት ይጀምራል ብሎ የነገረንም አልነበረም፡፡ (ቢነገረንስ ስናምን አይደል!) ግን ዕድሜ ለህልሜ! የኢንተርኔት አገልግሎት መጀመሩን በምስል አስደግፎ አሳየኝ፡ ከአሁን በኋላ ኢንተርኔት ብቻ ሳይሆን ሌላውንም የማምነው በህልሜ ሳይ ብቻ ነው፡፡ የትራንስፖርት እጥረት በሉት የመብራት መጥፋት፣ የመልካም አስተዳደር ችግር በሉት የኑሮ ውድነት ወዘተ… በዚህ በዚህ ጊዜ ይቀረፋል ተብሎ በኢቴቪ (EBC) ይሁን በጋዜጣዊ መግለጫ ቢነገር በጄ አልልም (“ካልታዘልኩ አላምንም አለች” አሉ!) በቃ በህልሜ እስከማይ ድረስ እጠብቃለሁ፡፡

(ህልሜ አይዋሽማ!) በነገራችሁ ላይ እነዚህ ችግሮች በእርግጥም ተፈተው ማየት የምትሹ ከሆነ፣ ሌላ ሌላውን ትታችሁ ህልማችሁን ብትጠብቁ ይሻላችኋል፡፡ የእናንተ ህልም እንደኔ ቀጥተኛ ሳይሆን ሰምና ወርቅ የበዛበት ቅኔ ከሆነ ደግሞ ለእኔ ፀልዩልኝ (ቶሎ በህልሜ እንዲታየኝ!) ግን አይገርምም---ከእውኑ ዓለም የህልም ዓለም መሻሉ! እኔ የምላችሁ… የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር ከሞቱ በኋላ ኢህአዴግ አካባቢ የተለወጠ ነገር አለ እንዴ? (በህልሜ እስኪታየኝ እኮ ነው!) ባለፈው ሳምንት እዚሁ ጋዜጣ ላይ ቃለመጠይቅ የተደረገላቸው ጉምቱው የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ፤ በመጪው ምርጫ ዙሪያ ከመንግስት ጋር ለመወያየት ጥያቄ አቅርበው ምላሽ እንዳልተሰጣቸው ጠቁመው፣“የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር ከሞቱ በኋላ በትንሹ የነበረው የመነጋገር ዕድል ተዘግቷል፤ እስካሁን ያየነው ነገር የለም” ብለዋል - በተስፋ መቁረጥ ስሜት (“በአገሬ ጉዳይ ተስፋ አልቆርጥም” ማለታቸውን አልዘነጋሁትም!) የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አንድ ታዋቂ ምሁር፣ የ2006 የጋዜጠኞችን እስርና ስደት በተመለከተ ሲናገሩ፤ “ኢህአዴግ ከጠ/ሚኒስትሩ ህልፈት በኋላ ደንግጧል” ብለዋል፡፡

የእኛ ነገር እኮ ግርም ይላል፡፡ በህይወት ሳሉ በተቃዋሚዎች ዘንድ አንዴም በበጎ ተነስተው የማያውቁት የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር፤አሁን እየተመሰገኑ ነው (“ሰው ካልሞተና ካልራቀ አይመሰገንም” አሉ!) በነገራችሁ ላይ --- ከእሳቸው ሞት በኋላ የመወያየት ዕድል ይጥበብ ይስፋ የሚያውቀው ኢህአዴግ ነው (የስነ-ምግባር ኮዱ አሁንም እያወዛገበ እኮ ነው?) ከቀድሞው ጠ/ሚኒስትር ህልፈት በኋላ ኢህአዴጎች ደንግጠዋል የሚለውም ጉዳይ ለእኔ ብዙ አልተዋጠልኝም፡፡ ቆይ ምንድነው የሚያስደነግጣቸው?! (ገዢ ነው ተገዢ የሚደነግጠው?) ህዝቡና አገሩ እኮ አልተለወጡም! እኔ ግን ምን ይመስለኛል መሰላችሁ? ኢህአዴግ ደንግጦ ሳይሆን ተለውጦ ነው፡፡ ለውጡ ለበጎ ይሁን ለክፉ ገና አለየለትም፡፡ እኔ የምለው--- ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ንግግራቸው ቁጣና ኃይለ ቃል ያዘለ አልሆነባችሁም ?(“የማይመቱት ልጅ ሲቆጡት ያለቅሳል” እንዳትሉኝ!) በሉ የቅርብ ጊዜ እቅዴን ልንገራችሁና ልሰናበት፡፡ በመጪው ግንቦት ወር አገራዊ ምርጫ ይካሄዳል፡፡ (የውጭ ታዛቢ አይኖርም ነው የተባለው?) እናም--- በምርጫው ማን እንደሚሳተፍና ማን “ፎርፌ” እንደሚሰጥ፣ ስለምርጫው ፍትሃዊነትና ዲሞክራሲያዊነት ወዘተ-- ለማወቅ የምርጫ ቦርድን መግለጫ አልጠብቅም፡፡ እኔ ያቀድኩት በህልሜ ለማየት ነው - እንደ ኢንተርኔቱ! ዘመኑ የህልም ነው!!

Saturday, 20 September 2014 11:05

“ግብረ ሰናይ ተግባር”

በ“ጆሲ” እና “ሰይፉ” ፕሮግራሞች ሲለካ!

          ኢቢኤስ ቴሌቪዥን፤ በቅርቡ “አወቃቀሬን አሻሽላለሁ” ብሎ “ኢብኮ” በሚል ስያሜ ብቅ ላለው ኢቲቪ፣ እንደ አማራጭ በመሆን የተለያዩ አዝናኝና አስተማሪና ዝግጅቶችን እያቀረበልን ነው፡፡ ተፎካካሪ ሊባሉ የሚችሉ ቶክሾዎችም የይዘትና ቅርጽ ልዩነት ሳይኖራቸው እንግዶቻቸውን እያቀረቡልን፣ ከስኬታቸውም ይሁን ከውድቀታቸው ትምህርት እየቀሰምን ነው፤ በሂደት ተመልካችን እንዳያሰለቹ ስጋት ቢኖረኝም፡፡ በተለይ ጆሲ እና ሰይፉ ሾዎች ፉክክሩ እያየለ ሲመጣ፣ ከተቋቋሙበት አላማ ውጪ በልዩ ልዩ የግብረ ሰናይ ተግባራት ተጠምደው መዋላቸው ሰርክ ተግባራቸው አድርገውታል፡፡ ጆሲ በዚህ በኩል የማንአልሞሽ ዲቦንና የአለባቸው ተካን ቤተሰቦች እንዲሁም ከሜሪ ጆይ የመጡ ሁለት ህጻናትን እንደደገፈና እንደረዳ ሲያበስረን፣ በዚህኛው ጎራ ደግሞ ሰይፉ ለዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ከሰጠው ሱፍ ልብስ ጀምሮ ለአባባ ተስፋዬ መኪና፤ ለአንድ ሀገር በቀል ግብረ ሰናይ ድርጅት ከ100 ደርዘን በላይ ደብተሮች ወዘተ ከስፖንሰሩ ጋር በመተባበር መለገሱን አሳይቶናል፡፡ ሁለቱ የቲቪ ቶክ ሾው አዘጋጆች፤ የፈጸሙት ተግባር በአርአያነቱ በጎ የሚባልና ሌሎች አቅሙ ያላቸው አርቲስቶች፤ ባለሃብቶች፤ ተራው ዜጋም ቢሆን በአቅሜ ምን ማድረግ አለብኝ ብሎ እንዲያስብ የሚያነሳሳ በመሆኑ እንደ መልካም ጅማሮ ቢወሰድ ክፋት የለውም፡፡

ለዚህ ጽሁፌ መነሻ የሆነኝን ሃሳብ የጫረብኝ ግን ጥድፊያና ሩጫቸው የተቸገሩትን ሰዎች ማገዝና መደገፍ ቢመስልም አላስፈላጊ ፉክክር ውስጥ ተዘፍቀው እየዳከሩ ይመስለኛል፡፡ ነገርዬው ልግስና ሳይሆን በልግስና መነገድ ነው የሚመስለው፡፡ ወደ ዝርዝር ጉዳዬ ከመግባቴ በፊት ግን philanthropist ለሚለው ቃል ፍቺውን ላቅርብና ሃሳቤን በጆሲ እጀምራለሁ፡፡ ታዲያ ይሄ የልግስና አስተሳሰብ (Philanthropic mentality) ድንገት የሆነ ሰአት ላይ የሚከሰት ሳይሆን ከልጅነት ጀምሮ በልቦናችን ውስጥ እያደገ,፣ እየጎለበተ የሚመጣ በጎ ሀሳብ ነው፡፡ ጆሲ ታዲያ እውነት የተቸገሩትን መርዳት የሚል የተሰበረ ልብ ካለው,፣ የቲቪ ዝግጅቱን በኢቢኤስ ማቅረብ እስኪጀምር ድረስ ምን አስጠበቀው? የመጀመሪያ አልበሙን ካወጣ እንኳን ወደ 10 አመት ገደማ አይጠጋም እንዴ? እስከ ዛሬ የት ነበር? ማንኛውም በጎ አድራጎት ተግባር ወይም ፋውንዴሽን ማቋቋም የፈለገ ግለሰብ፣ መነሻው የእርሱና የራሱ ጥሪት ነው፤ከዚያ መልካም ስራው ታይቶ ድጋፍና እርዳታ ሊያገኝ ይችላል፡፡ “ሜቄዶንያ”፤ “አረጋውያንን አንሱ”፤ “አበበች ጎበና”፤ ወዘተ የተባሉ ግብረሰናይ ድርጅቶችን ልብ ይሏል፡፡ ድጋፍ የተደረገላቸው ሰዎች በእርግጥም የተቸገሩ እንደሆኑ ከውስጣቸው ፈንቅሎ የሚወጣው እንባቸው ምስክር ነው፡፡ ምንም እንኳን የአለባቸው እህት ከወንድሟ ሞት በኋላ “የአለባቸው እህት ካሸር ሆና ሰራች እንዳይሉኝ ብዬ፣ ልጄ ትምህርት አቋርጣ እኔን እየረዳችኝ ነው” የሚለው አነጋገሯ ቀሽምና የሚያበሳጭ ቢሆንም፡፡

ለጆሲ ግን አንድ ጥያቄ ማቅረብ እፈልጋለሁ፡፡ አርቲስት መርዳት ያለበት አርቲስትን ብቻ ነው እንዴ? ሀገራችን ውስጥ ታላላቅ ስራዎችን የሰሩ፣ ነገር ግን ዛሬ ዞር ብሎ የሚያይ ሰው የሌላቸው የቀድሞ ጦር መሪዎች፤ መምህራን፤ የስፖርት ባለሙያዎች ወዘተ የሉም? በየሜዳው ሰብሳቢ ያጡ ህጻናት፤ አረጋውያን የሉም? እውነት የመረዳዳት ሃሳቡ ካለህ፣ እስቲ ያለህን ስምና ዝና ተጠቅመህ፤ የገንዘብ ድጋፍ አፈላልገህ፤ፕሮጀክት ቀርጸህ ወይም አስቀርጸህ የብዙዎች ችግር በዘላቂ ሁኔታ እንዲቀረፍ ለመትጋት ሞክር፡፡ መቼም ወታደርን ወታደር፤አስተማሪን አስተማሪ፤አርቲስትን አርቲስት ወዘተ ብቻ ይርዳ አይባልም፡፡ ሌላው ትዝብት የጫረብኝ ደግሞ የጆሲ አዲሱ አልበም ጉዳይ ነው፡፡ ከአልበሙ ሽያጭ 50 ከመቶ ለበጎ አድራጎት ይውላል ብሎ አወጀ፡፡ አልበም ማውጣትን ከበጎ ስራ ጋር ምን አገናኘው? አልበሙ ምርጥ ስራ ከሆነ (artistically) ስራው በራሱ አይወዳደርም ወይ? ኪነጥበብ ልትለካ የምትችለው በውስጧ የሚገኘው ውበት ያለው ፈጠራ፤ ነፍስን አሸፍቶ ስሙኝ ስሙኝ ስትል እንጂ በበጎ ስራ ካባ ተሸፍና ስትቀርብ አይደለም፡፡ የጥበብ ሥራና የበጎ አድራጎት ተግባር ሲደበላለቅ ውጤቱ ምን ሊሆን እንደሚችል ሆደ ቡቡ ወዳጆቼ ያሉት ነገር ጥሩ ማሳያ ይመስለኛል፡፡ “የጆሲን አልበምማ አሪፍ ባይሆንም እገዛዋለሁ” ይሄ ደግሞ በአበሻ ስስ ብልት ገብቶ አልበም መቸብቸብ ሆነብኝ፡፡

ብዙ ለማለት ባልሻም ከተነሳው ሃሳብ ጋር ተያያዥ ስለሆነው “ሰይፉ በኢቢኤስ ሾው” አንድ ሁለት ነገር ልበል፡፡ ሰይፉ ፣ የጆሲን ጅማሮ ቀድቶ፣ እኔም Philanthropist ሆንኩላችሁ እያለን ነው፡፡ የሱ ማስመሰል ደግሞ ይብሳል! በተለይ በአባባ ተስፋዬ ሽልማት ወቅት፣ በቃለ መጠይቁ ላይ የተስተዋሉ ተቃርኖዎች የሚያስተዛዝቡ ናቸው፡፡ ለምሳሌ “እኔ ወደ አሜሪካ ከመሄዴ በፊት” አለ ሰይፉ፤ “እኔ ወደ አሜሪካ ከመሄዴ በፊት አባባ ተስፋዬን ከኢትዮጵያ ህዝብ ምን እንደሚፈልግ በስልክ ጠይቄው “አሁን የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲያውቅልኝ የምፈልገው እግሬን ጉልበቴ ላይ እያመመኝ ስለሆነ፣ እንደ ምንም አዋጥተውም ቢሆን መኪና እንዲገዙልኝ ነው የምጠይቀው” ብሎ ስልኩ ተዘጋ፡፡ መቼም አባባ ተስፋዬን የሚያክል ታላቅ ሰው፣ (በሸገር የጨዋታ እንግዳ ከመዓዛ ጋር የነበራቸውን ቆይታ ጨምሮ በልዩ ልዩ ሚዲያዎች ያደረጉትን ቃለ ምልልስ አዳምጫለሁ) አንድ ህጻን ልጅ ማታ አባቱ ምን ይዞለት እንዲመጣ እንደሚፈልግ ሲጠየቅ፤ “ትልቁን ብሽክሊሊት” እንደሚለው አይነት ጥያቄ፣ ለኢትዮጵያ ህዝብ ያቀርባሉ ብዬ አልገምትም፡፡ ታዲያ ነገሩ ከየት መጣ ሊባል ነው? ራሱ ሰይፉ የእርሱንና የስፖንሰር አድራጊዎቹን ስምና ዝና ለማግነን የተጠቀመበት ተራ “እቃቃ ጨዋታ” ነገር ይመስለኛል፡፡ ሰው በድህነት ምክንያት የመደራደርና የመግደርደር አቅሙን ሲያጣ፣ እንደ አሻንጉሊት ልጫወትብህ ማለት እግዝሄሩም ቢሆን አይወደውም፡፡ አስገራሚው ነገር ደግሞ አባባ ተስፋዬ መድረክ ላይ ቀርበው “አሁን መኪናውን ምን ያደርጉበታል?” ሲላቸው “ያ በሽተኛው የልጅ ልጄ ትምህርት ቤት ይመላለስበታል” አሉ፡፡

አዲዮስ! የአባባ ተስፋዬ የእግር ህመምና የሰይፉ አስመሳይ የለጋሽነት ፍላጎት ተጋለጠ!! እናም ጆሲና ሰይፉ ሆይ፤ የቲቪው ፕሮግራም በፈጠረባችሁ ውድድር ምክንያት የተመልካችን ቀልብ ለመሳብ፣ ፕሮግራማችሁ ከተቋቋመበት አላማ ውጪ በሰዎች ማጣትና ድህነት ላይ ተንጠላጥላችሁ ከንቱ ዝናና ገንዘብ መቃረም ቢቀርባችሁ ይሻላል ባይ ነኝ፡፡ እውነት Philanthropist ነን ካላችሁ፣ ሃገራችን ውስጥ ታላላቅ የበጐ አድራጐት ስራዎችን ከፈጸሙት ግብረሰናይ ድርጅቶች ልምድ ውሰዱ፡፡ ሌላው ቢቀር በሙዚቃና ኪነጥበብ ሥራ ውስጥ ከሚገኘው ከታዋቂው የክቡር ዶክተር አሊ ቢራ ፋውንዴሽን ብዙ ተሞክሮ ማግኘት ትችላላችሁ፡፡ የአሊ ቢራ ፋውንዴሽን አርቲስቱ በራሱ ገንዘብ ያቋቋመው፤ የራሱ ቦርድና ስራ አስኪያጅ ያለው ሲሆን ትምህርት ባልተዳረሰባቸው የሀረር ቀበሌዎች ትምህርት ቤትን በማስገንባት ለትውልድ የሚተላለፍ አሻራ እያስቀመጠ ይገኛል፡፡ በተረፈ የራሳችሁን ስም ለማግዘፍ ስትሉ መድረክ ላይ ለይምሰል የምታፈሷትና የምታብሷት እንባ፣ የማስመሰል ነገር አለባትና እባካችሁ ልብ ይስጣችሁ!!

Published in ጥበብ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!

         እኔ የምለው…ግድግዳው ላይ ያለው ቀን መቁጠሪያ ተለወጠ? እኛ አገር ዘመን መለወጥ ማለት ግድግዳ ላይ ያለውን ቀን መቁጠሪያ መለወጥ ከሆነ እየሰነበተ ነዋ! የምር እኮ…ዘንድሮ “ሲጋራ አቆማለሁ…” “ቂማ አቆማለሁ…” “መጨለጥ አቆማለሁ…” የሚል አንድም ወዳጅ አልገጠመኝም፡፡ ወዳጆቼ ‘ሲፑ’ና ‘ቂማው’… ይሄን ያህል ተስማምተዋችኋል እንዴ! “ነገር እየሰማሁና እያየሁ ከምቃጠል ሳላይና ሳልሰማ እየቃምኩና እየጠጣሁ ብቃጠል ይሻለኛል!” ያልከን ወዳጃችን ጭራሽ እየወፈርክ ሄድክሳ! እውነትም “አለማየትና አለመስማትን የመሰለ ነገር የለም…” ምናምን የሚል የጥናት ውጤት የሆነ ቦታ ሊኖር ይችላል፡፡ ሀሳብ አለን…እንዲህ መፋጠጥ በተለመደበት ዘመን በየምግብ ቤቱ “ሌላው ተመጋቢ የሚመገበውን እየተንጠራሩ ማየት የተከለከለ ነው…” ምናምን የሚል ማስታወቂያ ይለጠፍልንማ!! ስሙኝማ…ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ሰዎቹ ምን የሚሉ ይመስለኛል መሰላችሁ… “አየሻት ስቴክ እኮ ነው የምትበላው!” “ታዲያ ስቴክ ብትበላ ምን አለበት?” “ምን አለበት! አንድ ብልቃጥ የጥፍር ቀለም ዓመት ተኩል የምታብቃቃ፣ ስቴክ የምትበላበት ከየት አምጥታ ነው! ይሄኔ አንዱን ሼባ ይዛ ይሆናል፡፡”

ሌላው ቡድን ዘንድ ደግሞ ምን ይባላል መሰላችሁ… “ስማ ያንን ችጋራም ምን እንደሚበላ አየኸው!” “ምንድነው የሚበላው?” “በእናትህ በቅዳሜ ምድር ክክ ምናምን ይበላል!” “የፈለገውን ቢበላ ምናለበት!” “የምን መፈለግ ነው! ችጋራም ነው እንጂ! የሚሠራው ቢዝነስ ቀላል መሰለህ! ልጄ ከሰዎቹ ጋር ተለጥፎ…” እናላችሁ…ልንመገብ ገብተን ስለሌሎች ተመጋቢዎች… “ከዕለታት አንድ ቀን…” ምናምን ታሪኮች የምናበዛ ሰዎች በርክተናል፡፡ የምር ግን…ነገሬ ብላችሁ እዩልኝማ…አሥር ጠረጴዛ ዘሎ ያሉ ሰዎች ያለ አጉሊ መነጽር እያሻገሩ አጎራረሳችሁንና አዋዋጣችሁን ‘ሲገመግሙ’ (ቂ…ቂ…ቂ…) እኔ የምለው…አጎራረሳችን የትኛው ካምፕ ውስጥ እንዳለን ያስነቃብናል እንዴ! ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… አዲስ አበባ በራሷ አነሳሽነት ነዋሪዎቿን ‘በመደብ’ እየለየች ነው፡፡

ልክ ነዋ…‘ንጥጥ’ ያሉ ሀብታሞች በተወሰኑ አካባቢዎች፣ ‘ምጥጥ’ ያሉ ቺስታዎች ደግሞ በየስርቻው! ሟርት አያስመስልብኝና እንዲህ አይነት ነገሮች እየበዙ በሄዱ ቁጥር የኋላ፣ ኋላ አሪፍ አይሆንም፡፡ ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…አሁን ‘የምንፈራው’ የሀብታሞቹን መኮሳተር (ለመኮሳተርስ ሲያዩን አይደል!) የጥበቃዎችን ግልምጫ ነው፡፡ ስሙኝማ…እግረ መንገዴን የሆነ ነገር ትዝ ብሎኝ ነው… አንዳንድ ሰዎች ‘መለዮ ሲለብሱና ዱላ ቢጤ መወዝወዝ ሲጀምሩ’ … አለ አይደል…የሚናፍቃቸው ዱላውን የሚያሳርፉበት ጀርባ ነው እንዴ! አሀ…በሰፈር ደረጃ ያሉ አንዳንዶቹን እኮ ስታዩዋቸው…አለ አይደል… በዓይናቸው እናንተን እያዩ በልባቸው… “ይሄ እንዲህ ትከሻውን እያሳየ የሚንጎማለለውን ቀልጥሞ፣ ቀልጥሞ መጣል ነበር!” እያሉ የሚያስቡ ይመስላችኋል፡፡

እና ‘መረጋጋት’ን የመሰለ ነገር የለም፡፡ ልክ ነዋ…ዱላው ‘እዛኛው እጅ’ ላይ የገባ ዕለት “…ይቅርታ እለምናለሁ፣ ጥፋቴን አውቄያለሁ…” ምናምን አይነት የአድማጮች ዘፈን ምርጫ አይሠራም! እኔ የምለው…ካወራን አይቀር…እዚቹ ከተማ ‘ጌትድ ኮሚዩኒቲስ’ የሚባሉ ግቢዎቹ ብቻ ሳይሆኑ ሙሉ መንደሮቹ ራሳቸው ግማሽ የእግር ኳስ ሜዳ በሚያካክሉ በሮች እየተከረቸሙ ነው፡፡ (ቀስ ብሎ ደግሞ ሙሉ አውራጃን ዓመት ሙሉ ቀጥ አድርገው ‘መቀለብ’ በሚችል ገንዘብ የሚገዙ መኪኖች በሚያልፉባቸው መንገዶች “ዝር ትሉና!” እንዳንባል መፍራት ነው!) እናላችሁ…ቀደም ሲል የመኖሪያ ግቢ በር ላይ ነው “ማንን ፈልገህ ነበር?” የምንባለው፡፡ አሁን ግን በታጠሩት መንደሮች ዋና በር ላይ ነው “ወዴት ነው!” የምንባለው፡፡ ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…በፊት እኮ የሀብታምና የድሀ መኖሪያ የሚለየው እንዲህ በመንደር ሳይሆን በቤቶቹ ትልቅነት ምናምን ነበር፡፡ እዚህ ጋ ቅልጥ ያለ ቺስታ እንደ ባለቤቷ ጠጅ ያንጋደዳት ጎጆ ውስጥ እየኖረ፣ ከፊት ለፊቱ ደግሞ የፊታውራሪ እከሌ የተንጣለለ ግቢ ይገኛል፡፡

(በነገራችን ላይ ፊትአውራሪ የሚለው መጠሪያ እየጠፋ መሄዱ የፊት አውራሪነት ባህሪይም አብሮ እየጠፋ ነው ማለት አይደለም፡፡ እንደውም ባይብስበት ነው!) እናላችሁ…ፈራንካው ያላቸው ሰዎች መንደሮቻቸውን በትላልቅ የብረት በሮች እንደሚዘጉት ሁሉ፣ ባለፈረንካዎችና ‘ባለድርሻ አካላቱ’ (ቂ…ቂ…ቂ…) በሁሉም በኩል ራሳቸውን በትላልቅ ‘የብረት በር’ እየከለከሉ ነው፡፡ ለምሳሌ…የፈረንካ ሰፈር ትኩስ ሀይሎች ሲገናኙ የሚያወሩት ምን ይመስለኛል መሰላችሁ… “ፌስቡክ ፍሬንዶቼ አራት ሺ ሰባት መቶ ሆኑ!” “ዋው! የእኔ ገና ሦስት ሺህ ናቸው፡፡ በቀደም ፍሬንድ የሆነችኝ…አንድ ምን የመሰለች ልጅ በፌስቡክ አግኝቻለሁ፡፡“ “ዩ ዶንት ሴይ! ከስቴትስ ነው?” “ኖ እዚሁ ነች…” “ኋት! ዩ ሚን ሺ’ዝ ሎካል!” “ብታያት እንዲህ አትልም ነበር፡፡ ምን የመሰለች ቺክ መሰለችህ! እንደውም ፕሮፋይል ፒክቸሯን ላሳይህ…” ከዛማ ሳምሰንግ ጋላክሲ ኤስ ፋይቭ ምናምን ይወጣል፡፡ ‘እዚህኛው ሰፈር’ ደግሞ ‘ፌስ’ ገና ከ‘ቡክ’ ጋር ሳይያያዝ ከሰው ልጅ አካል አንዱ የሆነበት ቺስታው መንደር ምን የሚባባሉ ይመስለኛል መሰላችሁ… “ስማ ከዚያች ልጅ ጋር እንዴት ናችሁ…” “የቷ!” “የቷ ትላለህ እንዴ! ያቺ ቀበሌ ሸማቾች ምናምን የምትሸጠው…” “ምን ታደርግ አንተ…እኔ ልጄ ስንት ሀሳብ አለብኝ! ሥራ ፍለጋ ስንከራተት ሁለት ዓመት እንዳለፈኝ አታውቅም!” “አትበሳጭ፣ ግዴለህም ለደግ ነው፡፡” “የምበላው እያጣሁ ለደግ…” ይልና መሀል ላይ ያቋርጣል፡፡ ‘ትርፍ’ ሊናገር ነበራ! አንድ ሁለቴ ያማትብና “…ይልቅ የማነበው አሮጌ መጽሐፍ ካለህ…” ምናምን እየተባለ ይቀጥላል፡፡እናላችሁ…እነሱ በ‘ቴክስት ሜሴጅ’ የፈለጉትን ቢባባሉ ያው የለመዱት ነው፡፡

እኛ ግን… አንዳንዱ የእኔ ቢጤ ‘ፋራ’ እንትናዬውን “ስዊቲ፣ አይ ላቭ ዩ ቬሪ ማች!” በሚል ሁሉም ሰው በሚገባው የፈረንጅ አፍ ግጥም አድርጎ ይጽፋል፡፡ አሀ…በእንግሊዝኛ ጥየቄ ማቅረብ ነገሩን ሁሉ ‘አሪፍ’ ያስመስለዋላ! ለነገሩ…“ስዊቲ!” “ሀኒ!” “ማይ ኤንጅል!” ምናምን ነገሮች በእኛ አፍ አያምሩማ! “ዳቦ ፍርፍር እየበሉ በእንግሊዘኛ ማወራት አያምርም…” የሚል ሰው የሆነ ቦታ ያለ አይመስላችሁም! (ስሙኝማ…አንዳንድ በፈረንጅኛ አፍ እንኳን የሚያነጥሱት ሰበሰቧቸው ቦታዎች ብቅ ማለታችን አይቀርም፡፡ እናላችሁ…በፈረንጅ አፍ ሲያወሩ ቋንቋው ላይ የሚያደርሱበት የኃይል ጥቃት ሶሪያና ኢራቅ አጠገብ ብንሆን ኖሮ ሌላ የዓለም ጦርነት ዋዜማ ሊሆን ይችል ነበር፡፡ አሀ… የአትክልት ተራ “ማዳም ጉድ ኦራንጅ…” አጠገብ እንኳን አይደርሱም! በዚህ ላይ ቅልጥ ያሉ ‘የብልግና’ ቃላት መሸለያ እየመሰላቸው ሲደጋግሙት ፈረንጅ ምን ያህል ይሳቀቅ ይሆን ያሰኛል! ከዓመታት በፊት በዕድሜ ‘ሲክስቲዋን’ ፉት ብለው ወደ ‘ሰቨንቲዋ’ የሚጠጉ እናት በ‘ታይታቸው’ ኋለኛ በኩል ‘ባይት ሚ’ (Bite me!) ተብሎ የተጻፈበት ለብሰው መሃል ከተማ ሲዘንጡ ማየቴ ትዝ ይለኛል፡፡ ብቻ ምን አለፋችሁ…በመንደር ትላልቅ በሮችም፣ በፌስቡክ ‘ፍሬንዶችም፣’ በ“ባይት ሚ” ምናምን አካሄዳችንም እያማረበት አይመስልም፡፡ የ‘ቦተሊካው’ ነገር አልበቃ ብሎ የሚለያዩን ነገሮች እየበዙ ሲሄዱ…አለ አይደል… ነገርዬው የትላልቅ በሮች ጉዳይ መሆኑ እንዳያበቃለት መፍራት ነው፡፡ከግቢ ‘በሮች’ ወደ መንደር ‘በሮች’…ተስፋ የሚሰጥ ‘ዕድገት’ አይደለም፡፡ ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል
  • 160 ባለሙያዎች ህክምና ሲሰጡ በኢቦላ ተይዘው፣ ግማሽ ያህሉ ሞተዋል
  • 2 ሺህ 46 ዜጎቿ በቫይረሱ ተይዘዋል፤ 1ሺህ 224 ሞተዋል
  • የአገሪቱ አጠቃላይ እንቅስቃሴ ተቃውሷል

         በላይቤሪያ በከፍተኛ ፍጥነት በመስፋፋት ላይ የሚገኘው የኢቦላ ቫይረስ፣ የአገሪቱን አጠቃላይ እንቅስቃሴ በማቃወስ ብሄራዊ ህልውናዋን አደጋ ላይ የጣለ ከፍተኛ ችግር የሆነበት አስከፊ ደረጃ ላይ መድረሱን ቢቢሲ ዘገበ፡፡የአገሪቱን የመከላከያ ሚኒስቴር ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ለ14 አመታት በዘለቀውና እ.ኤ.አ በ2003 በተቋጨው የእርስ በርስ ግጭት 250 ሺህ ያህል ዜጎቿ የሞቱባትና በመሰረተ ልማት አውታሮቿ ላይ ከፍተኛ ውድመት የደረሰባት ላይቤሪያ፣ አሁን ደግሞ ኢቦላ እንደ ሃገር መቀጠሏን ጥያቄ ውስጥ የሚከት የህልውና ፈተና ሆኖባታል፡፡ በቅርቡ በአገሪቱ የተቀሰቀሰው የኢቦላ በሽታ ከጊዜ ወደጊዜ በከፍተኛ ሁኔታ እየተስፋፋ መምጣቱን የጠቆመው ዘገባው፣ በበሽታው ከተጠቁ 2ሺህ 46 የአገሪቱ ዜጎች መካከል 1ሺህ 224 ያህሉ ተህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን ገልጧል፡፡“ኢቦላ ለላይቤሪያ ብሄራዊ ህልውና እጅግ አደገኛ ስጋት እየሆነ ነው፡፡ በፍጥነት በመሰራጨት ላይ የሚገኘው ይህ በቀላሉ የሚተላለፍ ገዳይ ቫይረስ፣ በአገሪቱ አጠቃላይ እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ ቀውስ ፈጥሯል፡፡” ብለዋል የላይቤሪያ የመከላከያ ሚኒስቴር ብሮዊን ሳሙካይ፣ ባለፈው ማክሰኞ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት አባላት ጋር ባደረጉት ውይይት፡፡

በሽታው በአገሪቱ ክፍተኛ ጥፋት እያደረሰ እንደሚገኝ የገለጹት ሚኒስትሩ፣ በቂ የጤና መሰረተ ልማት ያልተሟላላት የላይቤሪያ የጤና ተቋማት በበሽታው ተጠቂዎች መጣበባቸውንና ተገቢውን የህክምና አገልግሎት መስጠትና የቫይረሱን ስርጭት መግታት የማይቻልበት ደረጃ ላይ መደረሱን አስረድተዋል፡፡ አለማቀፉ ማህበረሰብ በላይቤሪያ ለተከሰተው የኢቦላ ችግር የሰጠው ምላሽ እጅግ አናሳ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ላይቤሪያ ከፍተኛ የሆነ የጤና መሰረተ ልማት አውታሮች፣ የህክምና ቁሳቁስ፣ የህክምና ባለሙያና የገንዘብ እጥረት እንዳለባት የገለጹት ሚኒስቴሩ፣ ይህም አገሪቱ በፍጥነት እየተሰራጨ ያለውን የኢቦላ በሽታ ለመግታት እንዳትችል እንዳደረጋት ተናግረዋል፡፡

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የላይቤሪያ ልኡክ በበኩሉ፣ የአገሪቱ የህክምና መስጫ ተቋማት በተገቢው ሁኔታ ያልተደራጁ መሆናቸው በቂ ህክምና ለመስጠት አለማስቻሉን ገልጾ፣ ተገቢውን ስልጠና ሳይወስዱና ጥንቃቄ ሳያደርጉ የህክምና ስራቸውን ሲያከናውኑ የነበሩ 160 የጤና ባለሙያዎች በሽታው መያዛቸውንና ግማሽ ያህሉም ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን አስታውቋል፡፡ላይቤሪያ ችግሩ ከተከሰተባቸው ሌሎች የምዕራብ አፍሪካ አገራት ጋር ሲነጻጸር፣ በሽታውን በመግታት ረገድ ይህ ነው የሚባል ተጨባጭ ስራ አለመስራቷን ጠቆሞ፣ በቫይረሱ የተጠቁ ዜጎችን ለማከም በጤና ተቋማት የአልጋ እጥረት መኖሩንም ገልጧል፡፡የአለም የጤና ድርጅትም፣ በላይቤሪያ የተከሰተውን የኢቦላ በሽታ ችግር ለመፍታት ትኩረት ሰጥተው በመስራት ላይ ለሚገኙ አለማቀፍ ድርጅቶች፣ የጀመሩትን ጥረት በሶስትና አራት እጥፍ እንዲሳድጉ ጥሪ አቅርቧል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

                     የቻይናውያን ባለሀብት ንብረት የሆነው ፀሐይ ሪል እስቴት፣ በየካ ክፍለ ከተማ ሲኤምሲ አደባባይ አጠገብ እየሰራ ያለውን የመኖሪያ ቤቶችና የንግድ ማዕከላት ሽያጭ በይፋ መጀመሩን አስታወቀ፡፡ ከዘጠኝ ወራት በፊት የተጀመረው የመኖሪያ ቤቶች መንደር ግንባታ 70 በመቶ በመጠናቀቁና ቀደም ሲል ቤት ለመግዛት የተመዘገቡ ሰዎች ለምን ሽያጭ አትጀምሩም እያሉ ስላስቸገሯቸው፣ የኢፌዲሪ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ፣ ከንቲባ ኩማ ደመቅሳና የቻይናው አምባሳደር ዢዢዮዋን ቤቶቹን መርቀው በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ ሽያጭ መጀመራቸውን የፕሮጀክቱ ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ ሚ/ር ይጆን ዋንግ በተለይ ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡ አዲስ አበባ፣ የአፍሪካ ህብረትና የተለያዩ የተባበሩት መንግስታት ድርጅቶች፣ ኤጀንሲዎችና የተለያዩ ዲፕሎማት መቀመጫ በመሆኗ፣ መዲናይቱን ዓለም አቀፍ ገጽታ ለማጎናፀፍና የነዋሪዎቿን የመኖሪያ መንደር ጥራት ደረጃውን የጠበቀ ለማድረግ ይህን የከተማ ውስጥ ከተማ ለመገንባት መነሳሳታቸውን ም/ሥራ አስኪያጅ ተናግረዋል፡፡ የከተማዋ ነዋሪዎች ያማረ ቪላ ሊኖራቸው ይችላል፡፡

ነገር ግን በሚኖሩበት አካባቢ ለኑሮ አስፈላጊ የሆኑ ነገሮች ተቀናጅተው አያገኙም፡፡ ለምሳሌ ሲኒማ ቤት ወይም የገበያ ቦታ ቢፈልጉ፤ በመኪና ከ30 ደቂቃ በላይ መጓዝ ሊኖርባቸው ይችላል፡፡ የእኛ ፕሮጀክት ሲጠናቀቅ ለኑሮ አስፈላጊ የሆኑ ነገሮች ተሟልተው ይገኛሉ፡፡ ባለኮከብ ሆቴል፣ ሲኒማ ቤት፣ ጂምናዚየም፣ የዋና ስፍራ፣ ትላልቅ የገበያ ማዕከላት (ሾፒንግ ሞልስ)፣ ሱፐር ማርኬቶች፣ መሰብሰቢያ አዳራሾች፣ ባንኮች፣ … አብዛኛው አስፈላጊ ነገሮች የተሟሉለት ይሆናል በማለት አስረድተዋል፡፡ የመኖሪያ መንደሩ 13 ህንፃዎች ሲኖሩት፣ ባለ 12 ፎቅ መሆናቸው ታውቋል፡፡ መንደሩ ከፊት ለፊት አራት ዋና ዋና የንግድ ማዕከላት ሲኖሩት እርስ በርስ የተገናኙ ባለሁለት ፎቅ ህንፃ እንዳላቸው ታውቋል፡፡ የመንደሩ ቤቶች ባለሁለት፣ ባለሦስት፣ ባለአራት ክፍሎችና እንግዳ ማረፊያ (ገስት ሩምስ) ሲኖራቸው ትልቅ አረንጓዴ ስፍራ፣ ፏፏቴ (ፋውንቴን ፑል)፣ ከህንፃው ስር መኪና ማቆሚያ፣ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች፣ ለሕፃናትና ለአረጋውያን የሚያስፈልጉ ቁሶች፣ … የተሟሉለት እንደሚሆን ሥራ አስኪያጁ ተናግረዋል፡፡

የፕሮጀክቱ አጠቃላይ ኢንቨስትመንት ከ1 እስከ 1.5 ቢሊዮን ዶላር (ከ20 እስከ 30 ቢሊዮን ብር) መሆኑን የጠቀሱት ሚ/ር ዋንግ፤ ባለፈው ታህሳስ ወር የተጀመረው የመኖርያ ቤቶች ግንባታ በዘጠኝ ወር 70 ከመቶው በመጠናቀቁ በቀጣዩ ሚያዝያ ወር የንግድ ማዕከላቱ ደግሞ በ2008 ዓ.ም ሙሉ በሙሉ ይጠናቀቃሉ ብለዋል፡፡ የቤቶቹ ዋጋ እንዳሏቸው ጥቅም (አድቫንቴጅ) የተለያየ መሆኑን የጠቀሱት ሚ/ር ዋንግ፤ አነስተኛው ዋጋ በካሬ ሜትር 22ሺ ብር፣ አማካይ ከፍተኛ ዋጋ 26ሺ ብርና ከዚያም በላይ ሊሆን እንደሚችል ገልፀዋል፡፡ በፀሐይ ሪል እስቴት ግንባታ 100 ቻይናውያንና ከ300-500 የሚደርሱ ኢትዮጵያውያን እየተሳተፉ መሆኑ ታውቋል፡፡

             በአዲስ አበባ የሚገኙ የግል ት/ቤቶች የተጋነነ የትምህርት ክፍያ ይጠይቃሉ የሚል አቤቱታ ያልቀረበባቸው ጊዜ የለም፡፡ በቅርቡ ግን መንግስትም ጭምር ለችግሩ ትኩረት የሰጠው ይመስላል፡፡ የመገናኛ ብዙሃን የመነጋገርያ አጀንዳም ሆኖ ሰንብቷል፡፡ እኔም ብዕሬን ያነሳሁት ይሄንን ርዕሰ ጉዳይ በተመለከተ ሃሳቤን ለመግለፅ ነው፡፡ ትምህርትን የማዳረስ ተግባር ትምህርት ለሀገራቸው ህዝብ በማዳረስ ረገድ መንግስታት ሊኖራቸው የሚገባውን የተሳትፎ ወሰን በመግለጽ በቀዳሚነት ሊወሳ የሚችለው እ.ኤ.አ በ1990 በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የማህበራዊና የባህል ምክር ቤት /UNESCO/ አማካኝነት የወጣው ትምህርት ለሁሉም አለማቀፍ መግለጫ /World Declaration on Education for All/ ነው፡፡ ሰነዱ 10 አንቀጾች ሲኖሩት፣ ሁሉም አንቀጾች መንግስታት በተለይ መሰረታዊ ትምህርት /Basic education/ በማዳረስ በኩል ሊኖራቸው የሚገባውን ሚናና የተግባር አቅጣጫ ያስቀምጣል፡፡ በዚህ ሰነድ አንቀጽ 3 ንዑስ አንቀጽ 1 መሰረት፤ ሀገራት መሰረታዊ ትምህርትን በእኩል ለማዳረስ እንቅፋት የሚሆኑ ጉዳዮችን ማለትም በራሳቸው ከፍለው መማር ለማይችሉ የህብረተሰቡ ክፍሎች፡- ለድሆች፣ ለጎዳና ተዳዳሪ ህፃናት፣ ለገጠሩ ህብረተሰብ፣ ለአርብቶ አደሮች፣ ለስደተኞች ወዘተ… ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር ቁርጠኛ አቋም ሊኖራቸው እንደሚገባ ተገልጿል፡፡

በሌላ በኩል ይህን የትምህርት ተግባራት ለማስፈፀም የሚያስፈልገውን ሀብት በተመለከተ ከመንግስት በተጨማሪ የግሉ ዘርፍና ለጋሾች ያላቸውን ገንዘብና የሰው ኃይል በማንቀሳቀስ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ማበርከት እንዳለባቸው ተጠቁሟል፡፡ እንደ ዓለም አቀፍ የትምህርት ደረጃ ምደባ /The International Standard Classification of Education/ መሰረት መሰረታዊ ትምህርት፤ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርትንና የሁለተኛ ደረጃ የአንደኛ ሳይክል ትምህርትን ያጠቃልላል፡፡ በታዳጊ ሀገሮች ደግሞ ከዚህም አልፎ የአፀደ ህፃናትና የጎልማሶች መሰረተ ትምህርትንም ያካትታል፡፡ ትምህርትን የሰብዓዊ መብት አካል አድርጎ የሚያወሳው ዓለማቀፍ የሰብዓዊ መብቶች መግለጫ /Universal Declaration of Human Right/ በበኩሉ፤ ትምህርት የሰው ልጆች መብት እንደሆነና መንግስታት ደረጃ በደረጃ የአንደኛ ደረጃ ትምህርትን በነፃ ማዳረስ እንደሚገባቸው፣ ዜጎችም የመማር ግዴታ እንዳለባቸው ያመለክታል፡፡ በአገራችን ህገ-መንግስት አንቀጽ 41 ንዑስ አንቀጽ 4 ላይ ደግሞ መንግስት ለትምህርት የሚያስፈልገውን ሀብት እንደሚመድብ ጠቅለል ባለ አገላለጽ ሰፍሯል፡፡ በሌላ በኩል ከሕገ-መንግስቱ ቀደም ብሎ በወጣው የሀገሪቱ አጠቃላይ የትምህርትና ስልጠና ፖሊሲ ላይም ዘርዘር ባለ መልኩ ተገልጿል፡፡ ትምህርትን ማስፋፋት በተለይም መሰረታዊ ትምህርትን ለሁሉም ማዳረስ እንደ አንዱ የፖሊሲው ዓላማ የተወሰደ ጉዳይ ነው፡፡

ጎልተው የወጡ የግል ት/ቤቶች ውጫዊ እና ውስጣዊ ችግሮች ከግል ትምህርት ቤቶች ጋር በተያያዘ ያለው ውጫዊ ችግር (“ውጫዊ ችግር” ከወላጆችና ከመንግስት አንጻር ያለውን ችግር ሲያመለክት፣ “ውስጣዊ ችግር” ከግል ትምህርት ቤቶቹ አንጻር ያለውን ችግር ያመለክታል) ትምህርት ቤቶቹ ከወላጆች አቅም አንጻር ከፍተኛ የትምህርት ክፍያ እያስከፈሉ ነው መባሉ ነው፡፡ ዋነኛው ውጫዊ ችግር ከፍተኛ ክፍያ መጠየቃቸው ቢሆንም ትምህርት ቤቶቹ ለዚህ የዳረጋቸው አስገዳጅ ውስጣዊ ችግር ወይም ምክንያት መታወቅ (መለየት) ያለበት ይመስለኛል፡፡ ከዚህ አንጻር በትምህርት ቤቶቹ በኩል በተደጋጋሚ እየቀረበ ያለው ምክንያት የሚያስተምሩበትና የሚሰሩበት የቤት ኪራይ፣ ለትምህርቱ ማስኬጃ፣ ለሰራተኞችና መምህራን ክፍያ የሚያወጡት ወጪ እየጨመረ መምጣት ነው፡፡ መንግስት በበኩሉ፤ የትምህርት ቤቶቹ የትምህርት ክፍያ ጭማሪ ብቸኛ ምክንያት ከፍተኛ ትርፍ የመሰብሰብ ዓላማ እንደሆነ ገልጿል፡፡ ለመሆኑ መንግስት በዚህ ጉዳይ ላይ መረጃ አለው? ለማንኛውም ከፍተኛ ክፍያው በትምህርት ቤቶቹ ወጪ መጨመር የተከሰተ ይሁን ወይም በከፍተኛ ትርፍ ፍለጋ በቅጡ ለይቶ ማወቅ ይገባዋል፡፡ አንድ ነገር ግን ግልፅ ነው፡፡ በት/ቤቶቹ የተጠቀሱት ችግሮች ሐሰት ናቸው የሚባሉ አይደሉም፡፡ የቤት ጉዳይ የከተማዋ ዋነኛ ችግር መሆኑ የታወቀ ነው፡፡

የግል ት/ቤቶችም በየጊዜው እየናረ የመጣው የቤት ኪራይ ዋጋ ሰለባ ከመሆን አይድኑም፡፡ እናም የትምህርት ክፍያ ጭማሪው በከፊል የቤት ኪራይ መናር ያመጣው ነው ቢባል ያሳምናል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ትምህርት ቤቶቹ በአብዛኛው ለመማር ማስተማር ሂደት የሚያስፈልጉትን መስፈርቶች (standards) ያላሟሉ እንደሆኑ ይነገራል፡፡ ትምህርት ቤቶች ከግለሰቦች በተከራዩዋቸው ጠባብ ግቢ ውስጥ ህፃናቱ ከወረቀትና ከጥቁር ሰሌዳ ጋር ሲፋጠጡ ውለው፣ ወደ ቤታቸው ይመለሳሉ የሚል አቤቱታም አለ፡፡ “ህፃናቱ የሚቦርቁበትና የሚሯሯጡበት ሜዳ የለም” ለማለት ነው፡፡ ምናልባት ያንን የምናገኘው በአዋጆች፣ በደንቦችና በመመሪያዎች ላይ ብቻ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ይሄም አንዱ የግል ት/ቤቶች ተግዳሮት ነው፡፡ ችግሩን ለመቅረፍ የመንግስት አካላት ተሳትፎ የግል ት/ቤቶች ከፍተኛ የትምህርት ክፍያን በተመለከተ ከመንግስት ወገን ጉዳዩ ያገባናል ብለው የተንቀሳቀሱት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ እና የንግድ ውድድር እና የሸማቾች ጥበቃ ባለስልጣን ናቸው፡፡ እነዚህ አካላት ችግሩን ለመቅረፍ በዋናነት ትኩረት ያደረጉት ደግሞ “ትምህርት ቤቶች ከፍተኛ ክፍያ ያስከፍላሉ” በሚለው ውጫዊ ችግር ላይ ብቻ ነው፡፡

በገሃድ እንደተመለከትነውም ችግሩን ለመፍታት የሄዱበት መንገድ፡- 1ኛ/ የመንግስትና የግል መገናኛ ብዙሃንን በመጠቀም የትምህርት ቤቶቹ ክፍያ የተጋነነና አግባብ አለመሆኑን በመንገርና በማስነገር ጫና (Lobby) ማድረግ፣ 2ኛ/ በክፍያው መጠን ላይ በወላጆችና በትምህርት ቤቶቹ መካከል ድርድር እንዲደረግ መግፋት፣ 3ኛ/ከፍተኛ የክፍያ ጭማሪ ባደረጉ የግል ትምህርት ቤቶች ላይ እርምጃ ለመውሰድ ምርመራ ማድረግ ናቸው፡፡ እነዚህ አካሄዶች በዋናነት ያተኮሩት ክፍያው ላይ እንጂ ለችግሩ መንስኤ የሆኑ ጉዳዮች ላይ አይደለም፡፡ እዚህ ላይ ግልፅ ሊሆን የሚገባው፣ መንስኤዎቹ ሳይፈተሹ ከፍተኛ ነው በተባለው ክፍያ ላይ ትምህርት ቤቶቹ ቅናሽ እንዲደርጉ ቢገደዱም እንኳን በመማር ማስተማሩ ሂደት ያሉትን ችግሮች ከመሰረቱ ሊቀርፈው የሚችል እውነተኛ መፍትሔ ሊሆን አይችልም፡፡ ሌላው ጥያቄ ደግሞ የንግድ ውድድር እና የሸማቾች ጥበቃ ባለሥልጣን፤ የትምህርት ጉዳይ ላይ እጁን ማስገባት ይችላል ወይ የሚለው ነው፡፡ ባለስልጣኑ የሀገሪቱን የነፃ ኢኮኖሚ ፖሊሲ መሰረት ያደረገ አመቺነት ያለው ነፃ የንግድ የገበያ ውድድር ሥርዓት እንዲፈጠር የሚያስችሉ ስራዎችን ብቻ እንዲሰራ ገደብ የተበጀለት እንደሆነየተቋቋመበት አዋጅ በግልጽ ያመለክታል፡፡ የባለስልጣኑ ተግባራት ለገበያ ውድድር ከተተዉ የግል ዕቃዎችና አገልግሎቶች /private goods & Services/ ንግድና ዝውውር ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ትምህርት ግን እንደግል ሸቀጥ /private goods/ ንግድና ዝውውር የሚቆጠር አይደለም፡፡

በተለይ የትምህርቱ ዓይነት መሰረታዊ ትምህርት (Basic Education) ሲሆን ደግሞ የገበያ ውድድር የሚለው ጉዳይ ጨርሶ የሚታሰብ አይሆንም፡፡ ይህን ስንመለከት ባለስልጣኑ በማይመለከተው ጉዳይ ጣልቃ ገብቶ እየሰራ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ የሸማቾች ጥበቃ ባለስልጣን ከዚህም አልፎ “ሕግን ተላልፈሃል” በሚል ምርመራ የማድረግ፣ እርምትና ቅጣትን የመጣል ሁሉ ሥልጣን ተሰጥቶታል፡፡ ይሄም በራሱ ተገቢነቱ ሊፈተሽና መፍትሄ ሊበጅለት የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ እንደማጠቃለያ በአብዛኛው እነዚህ ትምህርት ቤቶች የሚያስተምሩት ትምህርት መሰረታዊ ትምህርት (Basic Education) ተብለው በተፈረጁት ውስጥ የሚጠቃለሉ ናቸው፡፡ የመሰረታዊ ትምህርት ባለቤት ደግሞ መንግስት ነው፡፡ ከመንግስት ውጭ ያሉት የግሉ ዘርፍም ሆነ ሌሎች አካላት መሰረታዊ ትምህርትን በማስፈጸምና በማዳረስ የመንግስት አጋዥ እንጂ ባለቤቶች አይደሉም፡፡ መንግስት አጋዦቼ ናቸው ብሎ በጋራ እንስራ ለማለት ወይም አታስፈልጉኝም፤ በራሴ እወጣዋለሁ ሊል ይችላል፡፡ ይህን ለማለት የሚችለው ግን አገሪቱ ትምህርትን ለማዳረስ በቂ አቅም ሲኖራት ብቻ ነው፡፡ እውነታው ደግሞ ከዚህ በተቃራኒው ነው፡፡ አገሪቱና መንግስት ይሄ አቅም የላቸውም፡፡ ከዚህ አንፃር መንግስት ኢምንትም ቢሆን አስተዋጽኦ ሊያደርጉ የሚችሉ የግል ትምህርት ቤቶችን አልፈልጋቸውም ብሎ ከዘርፉ እንዲወጡ ሊያደርግ አይችልም፡፡ እንዲኖሩ መፍቀድ ብቻውን ግን በቂ አይደለም፡፡ መንግስት በዘርፉ የሚታዩትን ችግሮች በዘላቂነት በመፍታት፣ በጎ አስተዋጽኦዋቸውን ለማጎልበት የሚያበቁ እንቅስቃሴዎች ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡ ከእነዚህ የመንግስት እንቅስቃሴዎች አንዱ ለዘርፉ ድጎማ (subsidy) ማድረግ ሊሆን ይችላል፡፡ ድጎማው የግድ የገንዘብ ድጋፍ እንዲሆን አይጠበቅም፡፡

ድጎማው፣ ከመንግስት አንጻር ሲታይ ትምህርቱን ለማዳረስ ሊያወጣ ከሚያስበው ወጪ በተወሰነ መጠንም ቢሆን የሚቀንስለት፣ ከትምህርት ቤቶቹ አንፃር ደግሞ መሰረታዊ ውስጣዊ ችግራቸውን ለመቅረፍ የሚያስችላቸው ሊሆን ይገባል፡፡ ከዚህ አንጻር መንግስት የመሬት አቅርቦትና የታክስ ቅነሳ (ድጎማ) ማድረግን እንደ አንድ አማራጭ አይቶ መፈተሽ ያለበት ይመስለኛል፡፡ ችግሩን በዘላቂነት የሚፈታ ከዚህ የተሻለ አማራጭ አለ ከተባለም እሰየው ነው፡፡ ነገር ግን የችግሩን መንስኤ ለመመርመር ሳይሞክሩ በቅርቡ እንደታየው የግል ት/ቤቶች የሚያስከፍሉትን ከፍተኛ ክፍያ በማስቀነስ ላይ ብቻ መረባረብ ችግሩን ከመፍታት ይልቅ እንዳያባብሰው ያሰጋል፡፡ የግል ት/ቤቶች በሃይልና በጫና ክፍያቸውን እንዲቀንሱ ቢደረግ ለጊዜው ህብረተሰቡ እፎይ ሊል ይችል ይሆናል፡፡ ት/ቤቶቹ ግን ወጪያቸውን መቋቋም እያቃታቸው ከአገልግሎት ውጪ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ይሄ ደግሞ ሌላ ጥፋት ይሆናል፡፡

Published in ህብረተሰብ

    ኢትዮጵያ ጦርነት የሌለባት ሰላማዊ አገር በመሆኗ፣ ሕዝቧም ቀማኛ፣ ዘራፊና ነጣቂ ባለመሆኑ ኢትዮጵያን የምሥራቅ አፍሪካ ማዕከል አድርገን እየሠራን ነው ሲሉ የሊፋን ሞተርስ ሥራ አስኪያጅ ሚ/ር ፍራንክ (በቻይናዊ ስማቸው ሊዩ ጂያንግ) ገለፁ፡፡ ሚ/ር ፍራንክ ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረጉት ቃለ - ምልልስ፤ “የኢትዮጵያ ሕዝብ ጨዋ ነው፣ ስርቆት፣ ዝርፊያ፣ቅሚያና ነጠቃ የለበትም፡፡ ለዚህም ሕዝቡን፣ ደንበኞቻችንንና መንግሥትን በጣም እናመሰግናለን” ብለዋል፡፡ ወደፊት ወደ ምሥራቅ አፍሪካ ጐረቤት አገራት የመኪና ምርቶችን ለመላክ ኢትዮጵያን ማዕከል አድርገው ለመስራት ማቀዳቸውን በመግለጽም በዱከም ኢስተርን ዞን፣ በ400 ሚሊዮን ዶላር ዘመናዊ የመኪና መገጣጠሚያ ፋብሪካ እየገነቡ እንደሆነ አስታውቀዋል፡፡ እስካሁን 3,500 መኪኖች መሸጣቸውን የጠቀሱት ሥራ አስኪያጁ፤ ወደፊት እንደገበያው ሁኔታ በዓመት 5,000 መኪኖችና ከዚያም በላይ ለመገጣጠም ማቀዳቸውን ገልፀዋል፡፡

የዘንድሮው የመኪና ሽያጭ ገበያ በተለያዩ ምክንያቶች የጠበቁትን ያህል ባይሆንም ወደፊት እንደሚሻሻል የጠቆሙት ኃላፊው፤ ለገበያው አለመጨመር ዋነኛው ችግር ኢትዮጵያውያን ከአዲስ መኪና ይልቅ አሮጌ መግዛት ስለሚወዱ ነው ብለዋል፡፡ “አሮጌ መኪና የመጠቀሚያ ጊዜ ወሰን ስለሌለው አሁን በጐዳና ላይ የሚታዩት አብዛኞቹ አሮጌ መኪኖች ከ30 ዓመት በላይ ያገለገሉ ናቸው፡፡ በዚህም የነሳ የተቃጠለ ጋዝ በመልቀቅ አካባቢን ይበክላሉ፤ ከፍተኛ የድምጽ ብክለት ይፈጥራሉ፣ የመኪና አደጋ የመፍጠር ሚናቸው ከፍተኛ ነው፡፡ ከዚህም በላይ የአረንጔዴ ልማት ኢኮኖሚ ፖሊሲን ስለሚፃረሩ መንግሥት ትኩረት ሊሰጠው ይገባል” ሲሉ አሳስበዋል፡፡ የውጭ ምንዛሪ ችግር እንዳለባቸው ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፤ “የውጭ ምንዛሪ ችግር የለብንም፤ ምክንያቱም እኛ ወኪል ሳንሆን በ160 አገሮች ቅርንጫፍ ያለው የቻይናው ሊፋን ግሩፕ አካል ነን፡፡ ስለዚህ የውጭ ምንዛሪ እጥረት ሲኖር፣ ሌሎች ድርጅቶች ከ6 እስከ 8 ወር ሲጠብቁ፣ እኛ ከ15 ቀንና ቢበዛ ከሁለት ወር በላይ አንጠብቅም፡፡ ትንሽ ችግር የገጠመን በኤክሳይዝ ታክስ ነው፡፡

ለእኛ የተለየና ስሌቱም ግልጽ ስላልሆነ ትንሽ ቅሬታ ፈጥሮብናል፡፡ ነገር ግን ከገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት፣ ከኢንዱስትሪና ከውጭ ሚ/ር መ/ቤቶች ጋር እየተነጋገርንና እየተወያየን ስለሆነ በቅርቡ ውሳኔ እንደሚያገኝ ተስፋ አለኝ” ብለዋል፡፡ የመኪና መገጣጠሚያ ፋብሪካዎች እየበዙ ስለሆነ ውድድሩን እንዴት ለመቋቋም እንዳሰቡ ተጠይቀው፤ “የመኪና መገጣጠሚያ ፋብሪካዎች መጨመር አያስጨንቀንም፡፡ ምክንያቱም፣ አንደኛ በኢትዮጵያ ገበያ ለመቆየት ወስነን ከፍተኛ ካፒታል እያፈሰስን ነው፡፡ ሁለተኛ፣ በዘመናዊ መኪና ደረጃ ሊፋን ኢትዮጵያ ገበያ ውስጥ በመግባት የመጀመሪያው ብራንድ ነን፡፡ ከሌላ ኩባንያ ጋር ሆነን ኢትዮጵያ የገባነው በ2007 ቢሆንም ከ2009 ጀምሮ ለብቻችን መገጣጠም በመጀመር፣ ከሕዝቡ፣ ከደንበኞችና ከመንግሥት ጋር እንዴት መሥራት እንዳለብን የ7 ዓመት ልምድ አካብተናል፡፡ “ሌላው ደግሞ መኪና መሸጥ ብቻ ሳይሆን ከሽያጭ በኋላ የእኛን ያህል ሰርቪስ የሚሰጥ እንደሌለ ደንበኞቻችን ይመሰክራሉ፡፡ ለሰርቪስ ከሚያስፈልጉ ነገሮች አንዱ መለዋወጫ ነው፡፡ ምንም ዓይነት እጥረት እንዳያጋጥም ለመለዋወጫ 10 ሚሊዮን ብር መድበናል፡፡ በእነዚህ ሁሉ ደንበኞቻችን ይመርጡናል ብለን እናምናለን” በማለት አስረድተዋል፡፡

Page 6 of 14