በውጭ ምንዛሬ እጥረት ክፍያ በጊዜ አልደረሳቸውም

ዓለም አቀፍ ዝናን ያተረፉ የ”ፒስኩዌር” ሙዚቀኞች በክፍያ መጓተት ሳቢያ ዛሬ በአዲስ አመት ዋዜማ በሚሊዬኒም አዳራሽ ሊያቀርቡት የነበረው የሙዚቃ ድግስ ለሚቀጥለው ሳምንት መሸጋገሩን አዘጋጆቹ ገለፁ። ለዘፋኞቹና ለሙዚቃ ቡድናቸው በጥቅሉ 200ሺ ዶላር ገደማ በጀት ተይዞ እንደነበር ምንጮች የገለፁ ሲሆን
የዘፋኞቹ ክፍያ በዶላር እንደሆነ አዘጋጆቹ ጠቅሰው፤ ከባንክ የውጭ ምንዛሬ ለማስፈቀድ ጊዜ እንደፈጀባቸው ተናግረዋል፡፡
ዘግይቶም ቢሆን ክፍያው ለዘፋኞቹ ደርሷቸዋል፤ ነገር ግን፣ በአንድ ቀን ውስጥ ፈጣን ትራንስፖርት እንዲያገኙና እንዲመጡ ብዙ ጥረት ብናደርግም አልተሳካለንም ያሉት አዘጋጆቹ፣ ከፍተኛ የገንዘብ ኪሳራ ደርሶብናል ብለዋል፡፡
ከናይጄሪያዊያኑ ዘፋኞች ጋር በዋዜማው የሙዚቃ ድግስ በርካታ ኢትዮጵያውያን ሙዚቀኞችም እንደሚቀርቡ የሚታወቅ ሲሆን፤ ደንበኞች ትኬት የገዙት ሁሉንም ዘፋኞች ለማየት ስለሆነ ኢትዮጵያውያን ዘፋኞችን ብቻ ማቅረብ አንችልም ሲሉ አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡
ዛሬ ለደንበኞቻቸው መረጃ ለማቅረብና ይቅርታ ለመጠየቅ ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጡ የተናገሩት አዘጋጆቹ፣ የሙዚቃ ድግሱን ለመስከረም 11 ቀን እንዳሸጋገሩት ገልፀዋል፡፡
የዝግጅቱ ዋና ስፖንሰር ሜታ ቢራ ብዙ ወጪዎችን እንደሚሸፍን ምንጮች የገለፁ ሲሆን፣ የቲኬት ዋጋ እራትን ጨምሮ አንድ ሺ ብር ነው። በኮንሰርቱ አመልማል አባተ፣ ዘሪቱ ጌታሁን፣ ናቲማን፣ ጃሉድ፣ ታደለ ገመቹ፣ ፍቅርአዲስ ነቅአጥበብ፣ አብርሃም በላይነህ (ሻላይ) እና ተስፋዬ ታዬ ከመሃሪ ብራዘርስ ባንድ እና ከኩል ባንድ ጋር ይሳተፋሉ፡፡

Published in ዜና

ሳላዲን ሰኢድ
ዝነኛው የእግር ኳስ ተጫዋች ሳላዲን ሰኢድ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ባደረጋቸው 12 ጨዋታዎች 9 ጐሎችን አግብቷል፡፡ በዓለም ዋንጫ ማጣርያ እስካሁን አራት ጎሎችን ያገባው የ24 ዓመቱ ሳላዲን፤ደቡብ አፍሪካ ላይ አንድ፤ ሴንትራል አፍሪካ ሪፐብሊክ ላይ 3 ጎሎችን አስቆጥሯል፡፡ ሳላዲን በ300ሺ ዩሮ (ከ6ሚ ብር በላይ) የዝውውር ሂሳብ በኢትዮጵያ በከፍተኛ ዋጋ የተሸጠ የእግር ኳስ ተጫዋች ነው፡፡
መሠረት ደፋር
በዘንድሮ የሞስኮ የአለም አትሌቲክስ በ5ሺ ሜትር ለአገሯ ወርቅ ያስገኘችው ጀግናዋ አትሌት መሠረት ደፋር፤ ባለፈው ነሐሴ ወር በተካሄደው የ2013 የዳይመንድ ሊግ ውድድር በ5ሺ ሜትር ከአገሯ ልጅ አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ ጋር ተፎካክራ በማሸነፍ፣ የዳይመንድ ሊግ ዋንጫና 50ሺ ዶላር (1ሚ ብር ገደማ) ተሸላሚ ለመሆን በቅታለች፡፡
ጥሩነሽ ዲባባ
በዘንድሮው የሞስኮ የአለም አትሌቲክስ በ10ሺ ሜትር ውድድር አሸናፊ በመሆን ወርቅ ያጠለቀችው ጥሩነሽ ዲባባ፤ በዳይመንድ ሊግ ውድድር በአትሌት መሰረት ደፋር ተቀድማ ሁለተኛ በመውጣት የ5ሺ ዶላር (95ሺብር ገደማ) ተሸላሚ ሆናለች፡፡ ብዙም ሳትቆይ በቲልበርግ፣ ሆላንድ በተካሄደው 10ኪ.ሜ የጐዳና ላይ ሩጫ ተወዳድራም በአንደኝነት በማሸነፍ የወርቅ ባለድል በመሆን ዓመቱን በስኬት ቋጭታለች፡፡
መሃመድ አማን
በሞስኮው የአለም አትሌቲክስ በ800 ሜትር የወንዶች ውድድር አሸናፊ በመሆን የወርቅ ሜዳሊያ የተሸለመው መሃመድ አማን፤ በነሐሴ ወር በተካሄደው የዳይመንድ ሊግ ውድድር ድል በመቀዳጀት የዳይመንድ ሊግ ዋንጫና 50ሺ ዶላር (1ሚ ብር ገደማ) በማግኘት ተደራራቢ ስኬት አግኝቷል፡፡
የኔው አላምረው
በሞስኮው የአለም አትሌቲክስ የ5ሺ ሜትር ውድድር የፍፃሜ ተፋላሚ የነበረው የ23 ዓመቱ የኔው አላምረው፤ በርቀቱ የዳይመንድ ሊግ አሸናፊ በመሆን የዳይመንድ ሊግ ዋንጫና 50ሺ ዶላር (1ሚ ብር ገደማ) በመሸለም የዓመቱ የስኬት ፈርጥ ለመሆን በቅቷል፡፡

 

Published in ዜና

“ከበዓሉ ይልቅ ለልጆች የት/ቤት ወጪዎች ትኩረት መስጠት ይገባል”
*በግ ከ900 እስከ 3ሺ ብር *ሰንጋ በሬ 18ሺ ብር *ማኛ ጤፍ 2ሺ ብር

የዘንድሮው የአዲስ አመት ገበያ ከዚህ ቀደም ከነበሩት የበአል ግብይቶች ብዙም የተለየ አለመሆኑን የተናገሩ የበዓሉ ሸማቾች ፤ የሽንኩርት ዋጋ ግን አይቀመስም ብለዋል፡፡ በመዲናዋ ዋና ዋና ገበያዎች ሽንኩርት ኪሎው 16 ብር እየተሸጠ ሲሆን ካለፈው ዓመት ዋጋ ጋር ሲነፃፀር የ8ብር ጭማሪ አሳይቷል፡፡ ባለፈው አዲስ ዓመት ሽንኩርት በኪሎ ከ8 – 10 ብር እንደተሸጠ ይታወሳል። የሽንኩርት ዋጋ በእጥፍ የጨመረው ሽንኩርት ወደሚመረትባቸው አካባቢዎች የሚወስደው መንገድ በክረምቱ የተነሳ በመበላሸቱ እንደሆነ ነጋዴዎች ይናገራሉ።
ሰሞኑን በአዲስ አበባ ዋና ዋና የገበያ ቦታዎች ተዘዋውረን የአመት በዓል ገበያዎችን በቃኘንበት ወቅት የኑግ ዘይት አንደኛ ደረጃው በአማካይ 48 ብር በሊትር ሲሸጥ የነበረ ሲሆን ሁለተኛ ደረጃው 47 ብር ነው፡፡ ቅቤ አንደኛ ደረጃ በኪሎ 150 ብር ሲሸጥ ሁለተኛ ደረጃው 125 ብር፣ 3ኛ ደረጃው 120 ብር ይሸጣል፡፡ በርበሬ በአማካይ ኪሎው 65 ብር ሲሸጥ ሰንብቷል፡፡ እንቁላል በኤልፎራ ማከፋፈያዎች አንዱ 1 ብር 60 ብር ሲሸጥ፣ በሾላ ገበያ በ2 ብር፣ በሣሪስ ገበያ ደግሞ በ2ብር ከ75 ሲሸጥ ሰንብቷል፡፡
በተዘዋወርንባቸው የገበያ ስፍራዎች ተለቅ ያለ ዶሮ እስከ 180 ብር፣ መካከለኛው እስከ 120 ብር ሲሸጥ ተመልክተናል፡፡ በግ ትልቁ እስከ 3ሺ ብር ዋጋ የተቆረጠለት ሲሆን መካከለኛው 1700 ብር፣ አነስተኛ የሚባለው ደግሞ 900 ብር በመሸጥ ላይ ነው፡፡ ስለዓመት በዓል ገበያ የጠየቅነው የበግ እና የበሬ ነጋዴው ዮሐንስ ዘሪሁን ፤ ወቅቱ ክረምት በመሆኑ ከክልል አካባቢዎች በጐችን ማምጣት አስቸጋሪ እንደነበረ ገልፆ፣ ዋጋው ግን የተፈራውን ያህል አልጨመረም ብሏል፡፡ አብዛኛው ማህበረሰብ በመስከረም ወር የበግ እርድ የመፈፀም ባህል እንዳለውና መጪው የመስቀል በዓል በመሆኑ የበግ ተፈላጊነት ሊጨምር እንደሚችል ነጋዴዎች ተናግረዋል፡፡
በአብዛኞቹ ገበያዎች ፍየል ለሽያጭ ያልቀረበ ሲሆን ፍየል ባገኘንበት የሳሪስ ገበያ ሙክት ፍየል በ5ሺ ብር ሲሸጥ እንደነበር አይተናል፡፡ ፍየል የሌለበትን ምክንያት የጠየቅናቸው አንዳንድ ነጋዴዎች፤ በአዲስ አመት ከፍየል ይልቅ ብዙ የሚፈለገው በግ ስለሆነ ነው ብለውናል፡፡
የዓመት በዓልን የበሬ ገበያ ለማወቅ ከከተማ ወጣ ብሎ የሚገኘውን አቃቂ (ቄራ) የቃኘን ሲሆን ባለፈው ቅዳሜ በዋለው ገበያ፤ ሰንጋ በሬ እስከ 18ሺ ብር ሲሸጥ፣ መካከለኛው 12ሺ ብር፣ ወይፈኖች ደግሞ 7ሺህ ብር ተሸጠዋል፡፡ በሰሞኑ ገበያ የጤፍ ዋጋ ጭማሪ ማሳየቱን ነጋዴዎችና ሸማቾች ይናገራሉ፡፡ ተዘዋውረን በቃኘናቸው የገበያ ስፍራዎች የማኛ ጤፍ ዋጋ በአማካይ ከ2000-2100 ብር በኩንታል ሲሸጥ የሰነበተ ሲሆን ስንዴ ኩንታሉ ከ800-950 ብር ይገኛል፡፡ በሣሪስ ገበያ ለዓመት በዓል ሲሸምቱ ያገኘናቸው ወ/ሮ የኔነሽ መንበሩ፤ ኪሎው እስከ 200 ብር ደርሶ የነበረው ቅቤ አሁን በ150 ብር መሸጡ መልካም መሆኑን ጠቅሰው፣ አብዛኛው የወጥ አይነት የሚሰራበት ሽንኩርት 16 ብር በመግባቱ ለሌሎች ሸቀጦች የመደቡትን ገንዘብ ለሽንኩርት ለማዋል መገደዳቸውን ተናግረዋል። የሽንኩርት ዋጋ ለምን እንደተወደደ የጠየቅናቸው አንዳንድ ነጋዴዎች፤ የሽንኩርት ምርቱ ወደሚገኝባቸው አካባቢዎች የሚወስዱ መንገዶች በክረምቱ በመበላሸታቸው አቅርቦቱ ላይ ክፍተት በመፈጠሩ እንደሆነ ገልፀውልናል፡፡ የሽንኩርት ዋጋ በአብዛኛው ከክረምት ይልቅ በበጋ እንደሚጨምር አንዳንድ ሸማቾች ያለፈ ተመክሮአቸውን በመጥቀስ ይናገራሉ፡፡
የአዲስ ዓመት መጥቢያ የሆነው መስከረም ወር በአብዛኛው ቤተሰብ ዘንድ ወጪ የሚደራረብበት ወቅት እንደሆነ የሚታወቅ ሲሆን ወሩ የትምህርት መጀመሪያ በመሆኑ ከአውደአመቱ ገበያ በተጨማሪ ከትምህርት ቤት ጋር የተያያዙ ወጪዎች አቅምን ይፈታተናሉ፡፡
ለገሃር አካባቢ በጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ከተዘጋጀው ባዛር ለልጆቻቸው ጫማ ሲገዙ ያገኘናቸው አባት፤ ከበአሉ ይልቅ የልጆቻቸው የት/ቤት ቁሳቁሶች ማሟላት ላይ እንዳተኮሩ ይናገራሉ፡፡ “በአሉ በየአመቱ የሚመጣ ነው፡፡ ሌሎች በአሎችም ገና ይጠብቁናል። እንደኔ ልጆች ያላቸው የቤተሰብ ሃላፊዎች ከበአሉ ይልቅ ለልጆቻቸው አስፈላጊውን የትምህርት ቁሳቁስ ለማሟላት ቅድምያ መስጠት አለባቸው” ሲሉ የመከሩት እኚህ አባት፤ ለበአሉም ቢሆን እንደ ጐረቤታቸው ሳይሆን እንደ ቤታቸው የአቅማቸውን ማዘጋጀታቸውን ነግረውናል፡፡

Published in ዜና

50ሺህ ብር በጥሬ ገንዘብና 100ሺህ ብር ግምት ያለው ቁሳቁስ ተበረከተ
የተለያዩ ድርጅቶች ለመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን ማዕከል 50ሺህ ብር በጥሬ ገንዘብ ሲያበረክቱ 200ሺህ ብር ለመስጠት ቃል ገቡ፡፡ እንዲሁም 100ሺህ ብር ግምት ያላቸው የተለያዩ ቁሳቁሶች ተበረከቱ፡፡
ዜማ ብዕር የኢትዮጵያ ሴቶች ማኅበር የአዲሱን ዓመት መቀበያ ከመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን ጋር ለማክበር ጳጉሜ 3 ቀን 2005 ዓ.ም ባዘጋጀው ፕሮግራም የተሳተፉ ድርጅቶችና ግለሰቦች የተለያዩ ስጦታዎች በዓይነት የሰጡ ሲሆን 200ሺህ ብር ለመስጠት ቃል ገብተዋል፤ 50ሺህ ብር አሰባስበው ሰጥተዋል፡፡
ቼሬአሊያ ብስኩትና ዱቄት ፋብሪካ፣ ዲ ኤች ገዳ፣ አዲካ፣ ቢጂአይ የተለያዩ ቁሳቁሶች በዓይነት የሰጡ ሲሆን ሆም ቤዝ የእንጨት ሥራ 50ሺህ ብር ሰጥቷል፡፡ የአፍሪካ ጤና ኮሌጅ ደግሞ የተለያዩ አልባሳትና የፅዳት ቁሳቁሶች የሰጠ ሲሆን ያለማቋረጥ ሙያዊ ድጋፍ ለማበርከት ቃል ገብቷል፡፡
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ማኅበራት አንድ ሺህ ብር የሰጡ ሲሆን ጂኤም የወጣቶች ማዕከልና ሴንትራል ጤና ኮሌጅ የገንዘብ ድጋፍ ለማድረግ ቃል ገብተዋል፡፡
መቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን ማዕከል በአሁኑ ወቅት 200 አረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን እየረዳ ሲሆን፣ በአዲሱ ዓመት ደግሞ 200 ተጨማሪ ሰዎች ለመቀበል ተዘጋጅቷል፡፡

Published in ዜና

የአየር ኃይል ቬቴራንስ አሶስዬሽን እያስገነባ ላለው ባለ 4 ፎቅ ሕንፃ ማስጨረሻና የአየር ኃይሉን ታሪክ የያዘ መጽሐፍ ማሳተሚያ የገቢ ማሰባሰቢያ የእራት ፕሮግራም ማዘጋጀቱን አስታወቀ፡፡
የአሶስዬሽኑ ከፍተኛ አመራሮች በሰጡት መግለጫ፣ መስከረም 23 ቀን 2006 ዓ.ም ለሚደረገው የገቢ ማሰባሰቢያ፣ ክቡር ዶ/ር ሼክ መሐመድ ሁሴን ዓሊ አላሙዲ፤ ከ800 ሰዎች በላይ የሚይዝ አዳራሾችና እራት እንዲዘጋጅ መፍቀዳቸውን ገልጸዋል፡፡
በጥቂት ሰዎችና አውሮፕላኖች በ1937 ዓ.ም የተመሠረተው የኢትዮጵያ አየር ኃይል አኩሪ ታሪክ እንዳለው የጠቀሱት የአሶስዬሽኑ ሊቀመንበር ብ/ጀኔራል ተጫነ መስፍን፤ የአየር ኃይሉን የ68 ዓመት ታሪክ የያዘ መጽሐፍ ለማሳተም፣ የተለያዩ አገልግሎት መስጫ ክፍሎችና የአየር ኃይሉን የውጊያ ታሪክ በተንቀሳቃሽ ምሥል ለትውልድ ለማስተላለፍ፣ በቢሾፍቱ ከተማ እየተገነባ ላለው ባለ 4 ፎቅ ሕንፃ ማጠናቀቂያ የገንዘብ ችግር ስለገጠመው የገቢ ማሰባሰቢያ የእራት ምሽት መዘጋጀቱን ተናግረዋል፡፡
የመጀመሪያዋ አውሮፕላን በ1921 ዓ.ም በኢትዮጵያ ስታርፍ ብዙዎች ተደንቀው እንደነበርና ሥራቸውም መልዕክት ማስተላለፍ፣ አለቆች፣ ደጃዝማቾችና ራሶችን ማመላለስ እንደነበር የጠቀሱት ጀኔራል ተጫነ፤ ፋሲስት ኢጣሊያ አገራችንን በወረረች ጊዜ ቁጥራቸው 16 ቢደርስም የውጊያ ብቃት ስላልነበራቸው ሁሉም ማለቃቸውንና ዘመናዊ የአየር ኃይል በ1937 ዓ.ም በስዊድናውያን አሠልጣኝነት መቋቋሙን አብራርተዋል፡፡
አየር ኃይል ዘመናዊ ጄት አውሮፕላኖች ቢገዛም፣ የመጀመሪያዎቹ አብራሪዎች የአድዋ ድል የቀሰቀሳቸው ጥቁር አሜሪካውያን እንደነበሩ አንድ የአሶስዬሽኑ አባል ገልጸዋል፡፡ አየር ኃይሉ ከጊዜ ወደ ጊዜ አቅሙንና የውጊያ ብቃቱን በማሻሻሉ፣ ሁለት ጊዜ የሶማሊያን ወራሪ ኃይል ድባቅ በመምታት የአገሩን ሉዓላዊነት ማስከበሩን ሊቀመንበሩ አስረድተዋል፡፡
አፍሪካዊያን ስለ አውሮፕላን በቂ እውቀት ባልነበራቸው በ1950ዎቹ ዓመታት አየር ኃይሉ በነበረው የውጊያ ብቃት በተባበሩት መንግሥታት ተመርጦ፣ በኮንጐና በታንዛኒያ የሰላም ማስከበር ተልዕኮ መወጣቱን፤ የሱዳን፣ የናይጄሪያና የደቡብ የመን አየር ኃይል አባላት ማሠልጠኑን ሊቀመንበሩ አውስተዋል፡፡
በ1985 በቢሾፍቱ ከተማና አካባቢዋ የነበሩ የአየር ኃይል አባላት የመረዳጃ ማኅበር አቋቁመው ላለፉት 17 ዓመታት በከተማዋ ሰፊ እንቅስቃሴ በማድረግ፣ በቢሾፍቱ ከተማና አካባቢዋ ከ1ኛ እስከ 12ኛ ክፍል ከ1ኛ-3ኛ ለሚወጡ እንዲሁም ከ10ኛና ከ12ኛ ክፍሎች ከ1ኛ እስከ 3ኛ ለወጡ ተማሪዎች ሲሸልሙ መቆየታቸውን አንድ የአሶስዬሽኑ አባል ገልጸዋል፡፡
በመጨረሻም መረዳጃ ማኀበሩና የከፍተኛ መኮንኖቹ ተልዕኮ ተመሳሳይ ስለሆነ፣ አንድ ላይ ሆነው የአየር ኃይል ቬቴራንስ አሶስዬሽኑን መሥርተው እየተንቀሳቀሱ መሆኑን ብ/ጄኔራል ተጫነ መስፍን ተናግረዋል፡፡
በ2003 ዓ.ም የተመሠረተው የቬቴራንስ አሶስዬሽን በአሁኑ ወቅት 600 አባላት ሲኖሩት፣ አየር ኃይሉ ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ አገልግለው በተለያዩ ምክንያቶች በጡረታ የተገለሉ አሁንም በማገልገል ላይ ያሉና ወደፊትም የሚሰናበቱ አባላትን እንደሚይዝ ሊቀመንበሩ ገልጸዋል፡፡

 

Published in ዜና

የኢትዮጵያ አየር መንገድ እያስገነባ ላለው የሠራተኞች መኖሪያ ቤት ከፒቲኤ (ከፕሪፈረንሻል ትሬድ ኤርያ ወይም ከምስራቃዊና ደቡባዊ አፍሪካ የንግድና የልማት ባንክ) ጋር የ22 ሚሊዮን ዶላር ስምምነት ተፈራረመ፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ተወልደ ወ/ማርያም እንደጠቀሱት፣ አየር መንገዱ የሚያሰለጥናቸው ሙያተኞች የቤትና ትራንስፖርት አገልግሎት ወደሚሰጣቸው መካከለኛው ምስራቅ አገሮች መፍለሳቸውን ለመቀነስ 1‚192 ቤቶች እያስገባ መሆኑንና ለትራንስፖርት አቅርቦትም እያሰበበት መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ለሰራተኞቹ እየተሰሩ ያሉት ቤቶች ግንባታ 30 በመቶ መጠናቀቁንም ተናግረዋል፡፡
የፒቲኤ ባንክ ፕሬዝዳንት አቶ አድማሱ ታደሰ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአፍሪካም ሆነ በዓለም ከፍተኛ ዕድገት እያሳየ የመጣ ስምና ዝና ያለው በመሆኑ ብድሩን እንደሚከፍል በመተማመን የዳሬክተሮችና የማኔጅመንት ቦርዱ ብድሩን መፍቀዱ ገልፀዋል፡፡
ፕሬዝዳንቱ አክለውም ፣ባንኩ 29ኛ ዓመታዊ ጉባኤውን በኢትዮጵያ እያደረገ መሆኑን ጠቅሰው፣ ጉባኤው እዚህ እንዲሆን የተወሰነው ኢትዮጵያ የባንኩ መስራችና ከፍተኛ ባለአክሲዮን በመሆኗና እንዲሁም ኢትዮጵያ ፈጣን ኢኮኖሚ ከሚያስመዘግቡ 10 የዓለም አገሮች አንዷ በመሆኗ ኢኮኖሚውና የንግዱን ማህበረሰብ ለማነሳሳትና ለመደገፍ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ባንኩ እስካሁን በኢትዮጵያ ያደረገው የፋይናንስ ድጋፍ እዚህ ግባ የሚባል እንዳልሆነ የጠቀሱት ፕሬዝዳንቱ፤ የባንኩ ካፒታል እያደገ በመምጣቱ ፈጣን ኢኮኖሚያዊ ዕድገት እያስመዘገበች ካለችው ኢትዮጵያ ጋር መስራት የሁሉንም ወገኖች ዕድገት ከፍ እንደሚያደርገው ገልፀዋል፡፡
ፒቲኤ እስካሁን ለኢትዮጵያ አየር መንገድ 22 ሚ.ዶላር፤ ለሀበሻ ሲሚንቶ 50.5 ሚ.ዶላርና ለግሪን ኮፊ ኢንተርፕራይዝ 2.4 ሚ.ዶላር ብድር መስጠቱን ጠቅሰው፣ ወደፊት በአስመጪና ላኪ ዘርፍ ከተሰማሩ የንግዱ ማህበረሰብ ጋር ለመስራት ማቀዳቸውን ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

ዛሬ የምድብ 1 የሞት ሽረት ፍልሚያዎች በኮንጎ ብራዛቪል ሴንተራል አፍሪካ ሪፖብሊክ ከኢትዮጵያ እንዲሁም ደርባን ላይ ደቡብ አፍሪካ ከቦትስዋና በሚገናኙባቸው ጨዋታዎች ይደረጋሉ፡፡ በምድብ 1 የደረጃ ሰንጠረዥ ኢትዮጵያ በ5 ጨዋታዎች ምንም ሳትሸነፍ በ1 ጨዋታ በቅጣት 3 ነጥብ ተቀንሶባት በ10 ነጥብና በ1 የግብ ክፍያ ምድቡን ትመራለች፡፡ ደቡብ አፍሪካ በ8 ነጥብና በ4 የግብ ክፍያ 2ኛ ደረጃ ላይ ናት፡፡ ቦትስዋና በ7 ነጥብና በ1 የግብ ክፍያ ሶስተኛ ነች፡፡ የኢትዮጵያ ተጋጣሚ የሆነችው መካከለኛው አፍሪካ በ3 ነጥብና በ6 የግብ ዕዳ መጨረሻ ነች፡፡
ዛሬ ከመካከለኛው በአፍሪካ ሪፐብሊክ ጋር በኮንጎ ብራዛቪል የሚፋለመው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ባለፈው ሐሙስ ምሽት በኢንተር ኮንቲኔታል ሆቴል አሸኛኘት ሲደረግለት የአግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዚዳንት አቶ ሳህሉ ገብረወልድ ‹‹የፈፀምነውን ታሪካዊ ስህተት በታሪካዊ ድል በመመለስ ድሉን ለህዝባችን የአዲስ አመት ስጦታ እናደርገዋለን ›› ብለው የተናገሩ ሲሆን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በበኩላቸው ቡድናቸው ወሳኙን ጨዋታ አሸንፎ ለመውጣት የሚያስፈልገውን ዝግጅት እንዳደረገ፤ ተጨዋቾቻቸው በሙሉ ጤንነት ላይ እንደሚገኙ ገልፀዋል፡፡ የብሄራዊ ቡድኑ አምበል የሆነው ደጉ ደበበ ‹‹የህዝብ አደራ ተቀብለን እንደምንጓዝ እናውቃለን በድል አድራጊነት የተጓዝንበትን የ2005 ዓ.ም በድል እንደምናጠናቅቀው እምነቴ ነው›› ብሏል፡፡ ዋልያዎቹ ሞቃታማ የሆነውን የኮንጎ ብራዛቪል የአየር ጠባይ ለመላመድ በአዳማ ዝግጅታቸውን ሲያደርጉ ሰንብተዋል፡፡ ዋልያዎቹ በዛሬው ጨዋታ የሚኖራቸው ውጤታማነት አዲሱን ዓመት በታላቅ ተስፋ ለመጀመር ከማስቻሉም በላይ በሚቀጥሉት ሁለት ወራት ስፖርት አፍቃሪው ኢትዮጵያ በታሪኳ ለመጀመርያ ጊዜ ወደ የዓለም ዋንጫ የምታልፍበትን እድል በስፋት እንዲነጋገርበት ምክንያት ይሆናል፡፡
ጎል የተባለው የስፖርት ድረገፅ ከምድብ 1 የዓለም ዋንጫ የምድብ ማጣርያ የመጨረሻ ትንቅንቆች በፊት ከአንባቢዎቹ ድምፅ በማሰባሰብ ባወጣው ትንበያ በኢትዮጵያ እና መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ ጨዋታ ሙሉለሙሉ የአሸናፊነቱ ግምት ለዋልያዎቹ አድልቷል፡፡ ኢትዮጵያ ሴንተራል አፍሪካ ሪፖብሊክን 3ለ1 ታሸንፋለች ያሉት 30.1 በመቶ፤ 2ለ1 ያሉት 15.53 በመቶ እንዲሁም 2ለ0 ያሉት 14.56 በመቶ ናቸው፡፡ ለሌላው የምድቡ ጨዋታ በተሰጠ ግምት ደቡብ አፍሪካ ከቦትስዋና 1ለ1 አቻ ይወጣሉ ያሉትቨ 13.04 በመቶ ያህሉ ሲሆኑ 17.39 በመቶው 2ለ0 እንዲሁም 21.74 በመቶ 3ለ1 ደቡብ አፍሪካ እንደምትረታ ተንብየዋል፡፡
ዋልያዎቹ እና
የምድባቸው ቡድኖች ዝግጅት
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ባለፈው 1 ዓመት በዓለም ዋንጫው የ3 ዙር ማጣሪያዎች ባደረጋቸው 7 ጨዋታዎች አልተሸነፈም፡፡ በተጋጣሚዎቹ ላይ 11 ጐል አግብቶ የቆጠረበት 5 ነው፡፡ በእያንዳንዱ ተጋጣሚው ላይ በአማካይ 1.57 ጐል ያገባል፤ 0.71 ጐል ይገባበታል፡፡ በማጣሪያዎቹ በአጠቃላይ 12 ቢጫ ካርዶች የዋልያዎቹ ተጨዋቾች ተቀጥተዋል፡፡ ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከጋና ብሄራዊ ቡድን ጋር የወዳጅነት ጨዋታ የሚያደርግበት ግብዣ ከወር በፊት ቀርቦለት የነበረ ቢሆንም ብዙዎቹ ተጨዋቾች እረፍት ላይ በመሆናቸው እና ቅዱስ ጊዮርጊስ በኮንፌደሬሽን ካፕ ከነበረው ተሳትፎ በተያያዘ እድሉን ሳይጠቀሙበት ቀርተዋል፡፡ ከዚያ በኋላ ብሄራዊ ቡድኑ ለአቋም መፈተሻ የሚሆኑትን ሁለት የወዳጅነት ጨዋታዎች ከሱዳን እና ብሩንዲ ጋር ለማድረግ ጥያቄ ቢያቀርብም ምላሽ አላገኘም፡፡ የመካከለኛው አፍሪክ ሪፖብሊክ ቡድን ከኢትዮጵያ ጋር ከሚያደርገው ጨዋታ በፊት ለአቋም መፈተሻ የሚሆነውን ግጥሚያ ከሊቢያ ጋር በማድረግ 0ለ0 ተለያይቷል፡፡ ዛሬ ከሴንትራል አፍሪካ ሪፖብሊክ ጋር ለሚደረገው ወሳኝ ፍልሚያ ለዋልያዎቹ 23 ተጨዋቾች ተመርጠዋል፡፡ ከተለያዩ አገራት ለብሄራዊ ቡድኑ የተመረጡ ፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ሳላዲን ሰኢድ ከስኬርቴ ክለብ ቤልጅዬም፤ ጌታነህ ከበደ ከዊትስ ክለብ ደቡብ አፍሪካ፤ሽመልስ በቀለ ከአሊትሃድ ክለብ ሊቢያ እንዲሁም አስራት መገርሳ ከራህማት ክለብ እስራኤል ናቸው፡፡8 ተጨዋቾችን ለብሄራዊ ቡድኑ ያስመረጠው የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ነው ሲሆን ሳምሶን አሰፋ ፣ ሳላዲን በርጌቾ ፣አበባው ቡጣቆ ፣ቢያድግልኝ ኤልያስ፣ ምንያህል ተሾመ፣ በኃይሉ አሰፋ፣ አዳነ ግርማና ኡመድ ኡክሪ ናቸው፡፡ ከዘንድሮው የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን ደደቢት አምስት ተጨዋቾች ሲመረጡ እነሱም ሲሳይ ባጫ ፣ ብርሃኑ ቦጋለ ፣ስዩም ተስፋዬ፣ ዳዊት ፍቃዱ እና ማይክል ጆርጂ ናቸው፡፡ ቶክ ጀምስና ፋሲካ አስፋው ከኢትዮጵያ ቡና፤መድሃኔ ታደሰና ሽመልስ ተገኝ ከመከላከያ ፤ዮናታን ከበደና ደረጀ ዓለሙ ከዳሸን ቢራ፤ ሙሉዓለም መስፍንና አንተነህ ተስፋዬ ከአርባምንጭ ተመልምለዋል። የተቀሩት ሞገስ ታደሰ ከመድን፤ በረከት ይስሃቅ ከመብራት ሃይል፤ ተክሉ ተስፋዬ ከንግድ ባንክ ናቸው፡፡ባፉና ባፋዎቹ ለመጨረሻው የሞት ሽረት ትንቅንቅ በፕሮፌሽናል ቡድናቸው ተጠናክረዋል። 4 ተጨዋቾች ከእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ፣ ሁለት ወጣት አማካዮች ከሆላንዱ ኤር ዲቪዜ፣ ከፍተኛ ልምድ ያለው የቀኝ ተመላላሽ ከቤልጅዬም ክለብ እና ምርጥ የመሀል ተከላካይ ከሩስያ ፕሪሚዬር ሊጋ በመጥራት ሲሰሩ ቆይተዋል፡፡ ቦትስዋና በአመዛኙ በደቡብ አፍሪካ አብርሣ ፕሪሚዬር ሊግ በሚወዳደሩ ክለቦች ውስጥ ያሉ ከ10 በላይ ተጨዋቾች አሰባስባለች፡፡
የደቡብ አፍሪካው አሰልጣኝ ጐርደን ሌጀንሰንድ ከቦትስዋና ጋር በሚደረገው ጨዋታ በዓለም ዋንጫ ማጣሪያው ማናቸውንም ነፍስ የምንዘራበት ውጤት እና ሂሳባዊ ስሌትን ከቡድኔ እፈልጋለሁ ብለዋል፡፡ ከአጀማመር ይልቅ አጨራረስን ማሰብ ይሻላል ብለው የሚሰሩ አሰልጣኝ መሆናቸውን ሱፐር ስፖርት በዘገባው ገልጿል፡፡ ጎርደን ሌጀሰንድ አስተያየታቸውን ሲቀጥሉ ‹‹ቦትስዋናን ካሸነፈን በተከታታይ ካደረግናቸው 4 ጨዋታዎች 3 አሸንፈን ማለት ነው፡፡ ይህ በውድድር አንድ ብሔራዊ ቡድን ሊያገኝ የሚቻለው ከፍተኛ ውጤት ነው። ዋናው ነገር ቦትስዋን እንደምናሸንፍ እርግጠኞች መሆናችን ነው፡፡ በተቀረ መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ ኢትዮጵያን በማሸነፍ ትረዳናለች ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ” ሲሉ ተናግረዋል፡፡ የቦትስዋና ብሄራዊ ቡድን በሞግዚት አሰልጣኙ ስታንሌ ቶሶሄኔ የሚመራው ሲሆን በዛሬው ጨዋታ ቡድናቸው ያልተጠበቀ ድል ማስመዝገቡ እንደማይቀር እምነቴ ነው ብለው ተናግረዋል፡፡አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በጨዋታው ላይ አስተያየት ሲሰጡ‹ የሞት ሽረት ፍልሚያ ነው፡፡ ብሄራዊ ቡድናችን በፊፋ ቅጣት 3 ነጥብ በተቀነሰበት ሰሞን ከሩዋንዳ ጋር ለቻን ውድድር ለማለፍ የደረሰውን የደርሶ መልስ ትንቅንቅ በማሸነፍ ጥንካሬው ታይቷል፡፡ በተቀነሰብን ነጥብ ምክንያት ለደቡብ አፍሪካ እና ቦትስዋና በማጣርያው የማለፍ ተስፋን ፈጥሯል፡፡ ይሁንና በኛ ተጨዋቾች ያለው ጠንካራ መንፈስ ሙሉ ለሙሉ መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክን በማሸነፍ ላይ የሚያተኩር ነው። ሙሉ 3 ነጥብ በመውሰድ እናሸንፋለን። በማለት ተናግረዋል፡፡ የመካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ አሰልጣኝ የሆኑት ሄርቬ ሉጁዋንጂ‹‹ ብራዛቪል የገባነው ኢትዮጵያን ለማሸነፍ ነው፡፡ በምድቡ ሁሉም የሚገርፈው ቡድን የእኛ መሆኑን የሚያስቡ አሉ፡፡ ይህን አስተሳሰብ ፉርሽ ማድረግ እንፈልጋለን። በሁሉም የምድብ ጨዋታዎች ጥሩ ነበርን፤ ውጤት ያጣነው በእድለቢስነት ነው። ኢዮጵያን እናከብራታለን እንጅ እንፈራትም፡፡›› በማለት ለሱፕር ስፖርት አስተያየት ሰጥተዋል፡፡
አስሩ ምድቦች ያሉበት ሁኔታ
በዓለም ዋንጫ የተሳትፎ ታሪካቸው እስከ ሩብ ፍፃሜ በመድረስ የአፍሪካን ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገቡት ጋና እና ሴኔጋልን ጨምሮ 5 አገራት ዛሬ እና ነገ በሚደረጉ የመጨረሻ ዙር የማጣርያ ግጥሚያዎች ምድቦቻቸውን በመሪነት ጨርሰው ለማለፍ አንድ ነጥብ ብቻ የሚፈልጉ ናቸው። ጋና፤ ናይጄርያ፤ ሴኔጋል፤ ካሜሮንና ቱኒዚያ ምድቦቻቸውን በመሪነት ለመጨረስ በሜዳቸው በሚያደርጓቸው ጨዋታዎች አቻ ውጤት ይበቃቸዋል፡፡ በምድብ 1 ኢትዮጵያ ለማለፍ መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክን ማሸነፍ ግድ ይሆንባታል፡፡ የኢትዮጵያ አቻ መውጣት ለደቡብ አፍሪካ ቦትስዋናን አሸንፎ የማለፍ እድል የሚፈጥር ሲሆን መሸነፍ ደግሞ ደቡብ አፍሪካን ማሸነፍ ከቻለች ለቦትስዋናም ማለፍ ምክንያት ሊሆን ይችላል፡፡ በምድብ 2 ከፍተኛ የማለፍ እድል ያላት በ11 ነጥብና በ6 የግብ ክፍያ የምትመራው ቱኒዚያ ነች፡፡ ከምድብ 3 አይቬሪኮስት ማለፉ አረጋግጣለች፡፡ በምድብ 4 ጋና በ12 ነጥብና በ2 የግብ ክፍያ መሪነቱን ብትይዝም ዛምቢያ በ1 ነጥብ ብቻ ተበልጣ በተመሳሳይ የግብ ክፍያ እየተከተለች ነው፡፡ በምድብ 5 ኮንጐ በ10 ነጥብ 5 በ1 የግብ ክፍያ እየመራች ነው፡፡ ቡርኪናፋሶ በ9 ነጥብና በ4 የግብ ክፍያ እንዲሁም ጋቦን በ7 ብር በ5 የግብ ክፍያ የማለፍ ዕድል እንደያዙ ናቸው፡፡ በምድብ 6 ናይጄሪያ በ9 ነጥብና 3 የግብ ክፍያ ብትመራም ማላዊ በ7 ነበር በ3 የግብ ክፍያ እንዳደፈጠች ነው፡፡ ግብጽ ከምድብ 7 ከመጨረሻዎቹ ግጥሚያዎች በፊት ማለፏን ያረጋገጠችው በ15 ነጥብና በ5 የግብ ክፍያ በማስመዝገብ ነው፡፡ አልጀሪያ ደግሞ ምድብ 8ን በ12 ነጥብና በ4 የግብ ክፍያ ከ6ኛው ጨዋታ በፊት በመቆጣጠር ማለፏን አረጋግጣለች፡፡ በምድብ 9 መሪነቱን ካሜሮን በ10 ነጥብና በ3 በግብ ክፍያ ብትይዘውም ሊቢያ በ9 ነጥብና በ2 የግብ ክፍያ ትከተላታለች፡፡ በመጨረሻም በምድብ 10 ሴኔጋል በ9 ነጥብና 4 የግብ ክፍያ መሪነቱን ስትይዝ ኡጋንዳ በ8 ነጥብና 5 የግብ ክፍያ ተናንቃለች፡፡ በማጣሪያው የኮከብ ግብ አግቢነት ፉክክር በ5 ጐሎቻቸው ሦስት ተጨዋቾች ሲጠቀሱ፤ እነሱም ኢስማን ሱሊማን በ5 ጨዋታዎች 293 ደቂቃዎች በመጫወት፣ ጌታነህ ከበደ በ5 ጨዋታዎች 312 ደቂቃዎች በመጫወት እንዲሁም የግብፁ መሃመድ ሳላህ በ5 ጨዋታዎች 450 ደቂቃዎች በመጫወት ነው፡፡ ሌላው ኢትዮጵያዊ ሳላዲን ሰይድ በ4 ጨዋታዎች 347 ደቂቃዎችን ተጫውቶ ባስመዘገበው 4 ጐል ከሌሎች 7 ተጨዋቾች ጋር በማጣሪያው የኮከብ ግብ አግቢው ፉክክር የደረጃ ዝርዝር ተጠቅሷል፡፡
የ3ኛው ዙር የጥሎ ማለፍ
የዓለም ዋንጫው የመጨረሻው ጥሎ ማለፍ ትንቅንቅ የማጣሪያው 3ኛ ዙር ምዕራፍ ነው፡፡ በ2ኛው ዙር በምድብ ድልድል ላለፈው 1 ዓመት ሲደረግ በቆየው ፉክክር በአስሩ ምድቦች አንደኛ ደረጃ የያዙት 10 ብሔራዊ ቡድኖች ወደ ዓለም ዋንጫ የማለፍ ዕድላቸውን በደርሶ መልስ ጨዋታዎች ይወስኑበታል፡፡ ከምድብ ማጣሪያው የመጨረሻ 6ኛ ግጥሚያዎች በፊት ከምድብ 3 አይቬሪኮስት ከምድብ 8 ግብጽ እንዲሁም ከምድብ 9 አልጀሪያ ወደ 3ኛው ዙር ጥሎ ማለፍ መሸጋገራቸውን አረጋግጠዋል፡፡ ለቀሩት የ7 ብሔራዊ ቡድኖች ኮታ ዛሬና ነገ በሚደረጉ የምድብ ማጣርያው የመጨረሻ ፍልሚያዎች ይታወቃሉ፡፡ ኢትዮጵያ በዛሬው ጨዋታ ለዓለም ዋንጫ የመጨረሻ የጥሎ ማለፍ ማጣሪያ ከበቃች በውድድሩ የተሳትፎ ታሪክ ትልቅ ውጤት ይሆናል፡፡ በታሪካዊው የጥሎ ማለፍ ምዕራፍ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከአፍሪካ 10 ብሔራዊ ቡድኖች አንዱ ሲሆን ከምዕራብና ከሰሜን አፍሪካ ብሔራዊ ቡድኖች የሚገናኝበት እድል ያመዝናል፡፡ ከአይቬሪኮስት፣ ከጋና ወደ ከናይጀሪያ ወይም ከአልጀሪያ፣ ከግብፅ ወይም ከቱኒዚያ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ሊገናኝ ይችላል፡፡ የ3ኛው ዙር የጥሎ ማለፍ ድልድል ለ10ሩ ብሔራዊ ቡድኖች የሚወጣው ከሳምንት በኋላ በካይሮ ነው፡፡ አስሩ ብሔራዊ ቡድኖች ለጥሎ ማለፍ ድልድል የሚወጣላቸው በሁለት ማሰሮዎች ሆነው አምስት አምስት ሆነው በመቧደን ሲሆን በሁለቱ ማሰሮዎች የሚገቡት ቡድኖች ማንነትን የሚወስነው በሚቀጥለው ሰሞን በፊፋ ይፋ በሚሆነው ወርሃዊ የእግር ኳስ ደረጃ ነው፡፡የ3ኛው ዙር የጥሎ ማለፍ የደርሶ መልስ ጨዋታዎቹ ከወር በኋላ በኦክቶበር 11-15 የመጀመርያዎቹ ጨዋታዎች እንዲሁም ኖቬምበር 15-19 ላይ የመልስ ጨዋታዎቹ ይደረጋሉ። አፍሪካን ወክለው በ2014 እ.ኤ.አ ብራዚል ወደምታስተናግደው 20ኛው የዓለም ዋንጫ የማያልፉ 5 ብሔራዊ ቡድኖች በ3ኛው ዙር የጥሎ ማለፍ ትንቅንቅ ተለይተው ይታወቃሉ፡፡

Saturday, 07 September 2013 11:52

“መልክዐ ስብሐት”

ነገ ለውይይት ይቀርባል
በአርታዒ አለማየሁ ገላጋይ የተዘጋጀው “መልክዐ ስብሐት” ነገ ለውይይት እንደሚቀርብ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ አስታወቀ። “ስብሐትን ከሌላ ማእዘን” በሚል የትኩረት ሀሳብ መነሻ በማቅረብ ውይይቱን የሚመሩት አርኪቴክት ሚካኤል ሽፈራው ናቸው፡፡ ውይይቱ በብሄራዊ ቤተመፃህፍት ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ ለሦስት ሰዓት ይካሄዳል፡፡

የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የትያትር ትምሕርት ክፍል ለመክፈት በቅድመ ዝግጅት ላይ መሆኑ ታወቀ፡፡ ለዚሁ ቅድመ ዝግጅት ይረዳ ዘንድ የዩኒቨርሲቲው የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ትምሕርት ክፍል ምሁራን እና ሌሎች ጉዳዩ የሚመለከታቸው ኃላፊዎች፤ የሀገሪቱን ከፍተኛ የትምሕርት ተቋማት እየጎበኙ ነው፡፡ የአዲስ አድማስ ምንጮች የትምሕርት ክፍሉ በ2006 ዓ.ም የትምሕርት ዘመን እንደሚከፈት የገለፁ ሲሆን በዩኒቨርሲቲው የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነጽሑፍ አማርኛ ትምሕርት ክፍል ኃላፊ አቶ አማረ ተሾመ ግን “አንድ ባልደረባችን ባቀረቡት ፕሮፖዛል መሠረት የቅድመ መነሻ ሀሳብ ለማቅረብ በዝግጅት ላይ ነን፡፡ በትክክል መቼ እንደምንከፍት አልወሠንንም” ብለዋል፡፡

በራስ ሆቴል ትልቁ አዳራሽ እየቀረበ ያለው “ግጥም በጃዝ” 26ኛ ዝግጅቱን በመጪው ረቡዕ መስከረም ፩ እንደሚያቀርብ አዘጋጆቹ አስታወቁ። በረቡዕ ልዩ ዝግጅት አበባው መላኩ፣ ግሩም ዘነበ፣ ደምሰው መርሻ፣ ነቢይ መኮንን የግጥም ሥራዎቻቸውን ፋቡላ የኪነጥበባት ማሕበር “ከነፃ አውጪ” ባንድ ጋር በመሆን የሥነ ቃል ትርዒት ያቀርባሉ፡፡ ከቀኑ 11 ሰዓት ጀምሮ በሚቀርበው ዝግጅት የፍልስፍና ምሁሩ ዶር. ዳኛቸው አሰፋ ዲስኩር ያቀርባሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

Page 12 of 16