Friday, 13 September 2013 12:40

የአዲስ ዓመት ምኞት

ለአዲስ ዓመት የሆነ ስጦታ ማበርከት ያምረኛል። ስጦታ መስጠት የምፈልገው ደግሞ ለሁሉም ሰው ነው፡፡ “አርፈህ መልካም አዲስ አመት ይሁንልዎ! አትልም ምን ጣጣ ታበዛለህ?” እንደምትሉኝ ቢገባኝም/ቢሰማኝም…ይህ ግን የገፀ በረከት (ገፅ የማበርከት) ጥሜን አይቆርጥልኝም፡፡
ስለዚህ እስቲ ላስብ፡፡ ምን ልስጣችሁ?...የሀምሳ ብር የሞባይል ካርድ በየስልኮቻችሁ ላይ ልላክላችሁ? የሁላችሁንም የሞባይል ስልክ አላቀውማ…ምን ያደርጋል!…
አንድ ባለ አስር ብር ካርድ ገዝቼ፣ ፍቄ ቁጥሩን በመጣጥፌ ላይ አስፍሬ…ጋዜጣው ታትሞ ሲወጣ መጀመሪያ ጋዜጣውን የገዛ ሰው ቁጥሩን እንዲሞላ ለማድረግም አሰብኩ፡፡ ግን ጋዜጣውን መጀመሪያ የገዛ ሰው ሳይሆን ጽሑፉን መጀመሪያ ያነበበ ቢሞላውስ?..ቁጥሩን በሞባይላችሁ ላይ ስትጠቀጥቁ ልትውሉብኝ ነው፡፡
ቤቴ አልጋብዛችሁ ነገር፤ ስጦታዬን በዶሮ ወጥ መልክ ወይንም በቅልጥም መልክ እንድትግጡ… ሁለቱም (ቅልጥም እና ወጡ) እኔ ቤት የሉም፤ በዛ ላይ ቤቴ በጣም እሩቅ ነው፡፡ ከእናንተ ቤት አቅጣጫ በተቃራኒ ነው፡፡
ስለዚህ ስጦታዬ ዞሮ ዞሮ ቁስ የሆነ ወይንም ወደ ቁስ የሚመነዘር ነገር ሊሆን አይችልም፡፡ ያው ምኞት ብቻ ነው አቅሜ፡፡ ግን ምኞትም ከሆነ አይቀር…ከእውነተኛ የምኞት ምንጭ የፈለቀ፣ ፈልቆ እንደ ሀይላንድ ውሃ በፕላስቲክ እቃ ያልታሸገ፣ በሊትር ያልተወሰነ ነው ለእናንተ የምመኘው፡፡ ምኞቱ እናንተን ሁሉ የሚመለከት እንዲሆን ተመኘሁ። ለእግዜር ጆሮ ቀለል ያለ ምኞት ራሱ ማግኘት ቀላል አይደለም፡፡ አሁን ለምሳሌ ለሁላችሁም ስኬታማ አመት ብመኝ…ፈጣሪ ራሱ አይሰማኝም። ከልብ የመነጨ ምኞት አይደለም፡፡ ቅዥት ነው፡፡ የሚጨበጥበት ቦታ የለውም ምኞቱ፡፡
አሳዳጁ ጭራውን እንኳን አይዘውም፤ ምኞቱን ለማሳካት የሚያሳድደው መንግስት ሊሆን ይችላል። ወይንም ፈጣሪ፡፡ ወይንም እድል፡፡ ወይንም ግለሰብ፣ እድል እና ፈጣሪ፡፡
ስለዚህ ለሁላችሁም ስኬት ልመኝላችሁ ብችልም…አላደርገውም፡፡ ባደርገውም የተመኘሁት አይሳካም፡፡ እንደዚህ ብዬ ምኞቴን አሻሽዬ ልመኝ:- “ስኬት ለሚገባችሁ ይሳካላችሁ”
ምኞት ወደ ተጨባጭነት ቀረብ ሲል “ስጦታ” ተብሎ መጠራት ይችላል ባይ ነኝ፡፡ “የመስራት አቅም እና ፍላጐት ያላችሁ…ስራ ያሰራችሁ፤ ስራ መስራት እየሰነፋችሁ ስራ የምታስሱም እንደፍጥርጥራችሁ!…ተቻችሎ መኖር የሚያምራችሁ የምትችሉት እና የሚችላችሁ ይስጣችሁ (ነገር ግን መቻቻል እያማራችሁም ከዚህ በፊት ሊሳካላችሁ ካልቻለ…አርፋችሁ ራሳችሁን እንድትችሉ ምኞቴ ነው)፡፡
ስጦታዬ ቀጥሏል፡፡ ርካሹ ስጦታ ምኞት ነው፡፡ ወደ ኪስ አይገባም…አይወጣምም፡፡
“የሚያታልሉ ሰዎች ያታለሉትን ያህል (እምነት፣ ገንዘብ፣ እውነት) ከቁመታቸው ላይ ይቀነስባቸው” ብዬ ልመኝ ነበር፡፡ ከአፌ መለስኩት፡፡ እቺን ስጦታ ማንም ሰው ስለማይቀበለኝ ተውኳት፡፡ ማንም አይቀበለኝም፤ ማንም በቁሙ ቁመት ይዞ አይገኛትማ፡፡ ምኞቴ ቢሳካ፡፡
ስለዚህ ምኞቴን አሁንም አሻሽለዋለሁ፡፡ “የሚያታልሉ ሰዎች የሚያታልሉበትን ምክንያት ይወቁት፡፡ በማታለል ምንም ትርፍ ላያገኙ የሚያጭበረብሩ ሰዎች “እግዜር ያይላቸው” ዘንድ ምኞቴ ነው፡፡ መፍትሔ ለሌለው ነገር “እግዜር እንዲያይ” መመኘት ብቻ ነው መፍትሔው፡፡
“በጐቹ እና ፍየሎቹ እንደዚሁም በሬዎቹ ለአመት በአል ለለውጥ (በነጋዴዎቹ ፋንታ) የራሳቸውን የስጋ ተመን አፍ አውጥተው እንዲመሰክሩ ምኞቴ ነው” ተገዝተው መታረዳቸው ካልቀረ ቢያንስ ቢያንስ ምናለ ዋጋቸውን ከመሞታቸው በፊት ራሳቸው ቢናገሩ? ግን ይሄም የማይመስል ምኞት ነው፡፡ “ምናለ ሳልወለድ በቀረሁ ኖሮ” ከሚል ምኞት የተለየ አይደለም፡፡ እሽ እንደፈረደብኝ ላሻሽለው “የበጐቹን ዋጋ መንግስት፣ ነጋዴ እና የበጉ የስጋ ክብደት (ከሚዛን ጋር ሆነው) ሶስቱ ተማክረው ቢነግሩዋችሁ እመኛለሁ”
“ይሄ ‘የኑሮ ውድነት’ የሚባለው ሰውዬ ቢሞት እመኛለሁ” ካሁኑ… እኔ እየተመኘሁ ኔትወርኩ ሲጨናነቅ ተሰማኝ፡፡ ኔትወርኩ የተጨናነቀው በእኔ እና በእናንተ ፀሎት ብቻ አይደለም፡፡ መንግስትም እንደኛው እየተመኘ ነው፡፡ ማድረግ የሚችለውም የማይችለውም የሚመኝ ከሆነ…ምን ዋጋ አለው፡፡ ዲያስፖራ ከእኔ እኩል ኮንዶሚኒየም ለማግኘት እየተመኘ እኮ ነው…የፀሎት ኔትወርኩ የተጨናነቀው፡፡
“ሁሉ ሰው ቤት እንዲኖረው እመኛለሁ”…ግን ለሁሉ ሰው ቤት መስሪያ የሚበቃ መሬት መኖሩን እርግጠኛ ባልሆንኩበት ደረጃ ይሄንን መመኘቴን እቃወማለሁ፡፡ “የማይሆኑ ምኞቶችን የሚቃወም የፖለቲካ ፓርቲም እንዲመሰረት እመኛለሁ”
ሁሉም ሰው መኪና እንዲኖረው አልመኝም፡፡ ሁሉም ሰው መንገድ ይሰጠኝ “ይሰየምልኝ” ማለቱ ስለሚያሰጋኝ ነው፡፡ በዛ ላይ መንገዶቹ ተሰርተው ሳያልቁ የትራፊክ ፖሊስን ስራ ጫና ከመጨመር ውጭ ሌላ ትርፍ አይታየኝም፡፡
“ሁሉ ሰው ሶስቴ መብላት ሲችል ቢያንስ አንዴ እንዲጠግብ እና ሲጠግብ እርስ በራሱ እንዳይመቀኛኝ እመኛለሁ” ምቀኝነት ራሱ ለብዙ ዘመን በመሐላችን እየኖረ ማንም ሊይዘው ያልቻለ ሽፍታ ነው፡፡ የጥንት ሽፍታ ነው፡፡ ከትውልድ ትውልድ አቅሙ የማይደክም፡፡
አመት በአል የሚከበረው በልጆች ምክንያት እንደሆነ ማመን ጀምሬአለሁ፡፡ “የአመት በአል መንፈስ ለመፍጠር ስንል ወደ ቤተሰብ ምስረታ (baby farming) ያለ በቂ ዝግጅት እንዳንገባ እመኛለሁ” ትዳር በቀላሉ የኮንዶሚኒየም ቤትን ከማግኘት ጋር ሲመሰረት ተመልክቻለሁዋ፡፡ “አንድ ስቱዲዮ እና ሁለት ልጆች አሉኝ” የሚሉ ጐረምሳ አባቶች እየበዙ ነው፡፡ የህዝብ ቁጥር መጨመር ትርፍ ሰዎችን (እንደ ሰሞነኛ የታክሲ አጫጫን) እንዳይፈጥርብን እመኛለሁ”
“ቅንነት በሀገሬ ሰዎች ላይ እንዲሰፍን እመኛለሁ”…እንደዚህች አይነቷን ምኞት ሲናገሩ የምሰማቸው ሰዎች ብዙውን ጊዜ ቅንነት የጐደላቸው ወይንም ቅን ሆነው የማያውቁ ናቸው፡፡ እቺን የአሁኗን ምኞቴን ስቃችሁ እለፏት፡፡ ቅንነት በውስጥ ከሌለ ከውጭ አይመጣም፡፡ እንደ ኑሮ፤ ወይንም የሰውነት ውፍረት… ሀገር በመቀየር፣ ሃይማኖት በማጥበቅ ቅንነት አይገኝም፡፡
ሰላም ልመኝላችሁ?...ግን የትኛውን አይነት ሰላም? የራሳችሁ ህይወት ሲስተካከል ወይንም ከማዕበሉ ሲያመልጥ የምታገኙትን ሰላም? ሰላም ባላችሁበት? የትም የሌሉ ሰዎች ሰላም እንዲያገኙ ምኞቴ ሰፋ ማለት አለበት፡፡
በሌላ ሰው መሰበር የሚቃና አንገት፤ ሰላምን አግኝቻለሁ የሚለኝ ከሆነ ሰላምን እንዲሁ በደፈናው ለመመኘት እፈራለሁ። (በዚህ አመት) ከስራው የሚባረር/የሚታገድ ጓደኛውን ቦታ የወረሰ ሰው፣ “ሰላም አግኝቻለሁ” ካለኝ በእኔ ምኞት ምክንያት እንዳልሆነ ንገሩልኝ፡፡
“ሁሉም ህፃናት ይደጉ፤ ርሃብ ወይንም ሐዘን አይንካቸው፤ የፈለጉት ሁሉ ይሟላላቸው…ደስተኛ ይሁኑ” እቺ ምኞት ላይ ብቻ በጣም እርግጠኛ ነኝ፡፡ ፈጣሪም፣ መንግስትም፣ እግዜርም፣ ወላጆችም ይሄን ምኞት ለመሙላት ጐን ለጐን የሚሰሩ ይመስለኛል፡፡
በእርግጥም ስጦታዬን ማበርከት የምወደው ለህፃናቱ ነው፡፡ የዘመን መለወጥም ሆነ አዲስ ሆኖ መምጣት ለአዋቂዎቹ ሳይሆን ትርጉም የሚሆነው ለህፃናቱ ነው፡፡ ለአበቦቹ፡፡ ለጐረምሳ እና አዋቂ ወላጆች ለህፃናቱ የተመኘሁት ምኞት በሚያሳድጓቸው አበቦች በኩል ይደርሳቸዋል። ይድረሳቸው፡፡
መልካም አዲስ አመት!

Published in ህብረተሰብ

የዛሬ አሥር ዓመቱን ዘመን መለወጫ በዓል የማስታውሰው ከአንዲት ባተሌ ድመት ጋር አዳብዬ ነው፡፡ እዚህ ትውስታ ውስጥ ደራሲ ስብሐት ገብረእግዚአብሔርም አለበት። ያኔ ድመቷና እሱ መካኒሳ አቦ አካባቢ ጉርብትና በማጠናከር ላይ ነበሩ፡፡ ስብሐት የተከራየው ሙሉ ግቢ ውስጥ ማን እንዳከራያት ያልታወቀች ባተሌ ድመት በአጥሩና በቤቱ ቦለኬት መካከል ተወሽቃ ትኖራለች፡፡ አውሬ ናት፤ ሰው ስታይ ከቻለች ከአካባቢው ትጠፋለች፣ ማምለጫ ካጣች ክፉኛ ትቆጣለች፡፡
“ተውዋት አርበኛ ናት” ይላል ስብሐት በቀልድ። አትንኩኝ ባይነቷ ብቻ ሳይሆን መጐሳቆሏም የአርበኛ ነው፡፡ ቢጫ ነብርማ መልክ ቢኖራትም አዘውትሮ ስለሚርባት ውበት ከእርሷ እርቋል፡፡ ቆዳዋ ከአጥንቷ ጋር ተጣብቆ ሙግግ ያለ አንገት አላት፡፡ ሲያይዋት የምትቀፍ ብትሆንም ስብሐት ስለእሷ አዘውትሮ ይጨነቃል፡፡
“አካባቢውን በሞኖፖል ከያዘው ፍጡር ጋር ተጣልታ፣ ህይወት እቅጯን መከራ ብቻ ሆነችባት” ይላል፡፡
“እንዴት?” ሲባል
“ምን እንዴት አለው? ከተማ ላይ እኮ ፈላጭ ቆራጩ፣ ሰው ነው፡፡ ቢሰጥም ቢነሳም የሚችል አምላክ ልትለው ትችላለህ፡፡
ታዲያ ይቺ አርበኛ ሰው አይንካኝ የምትል አውሬነት ውርሷ ሆኖ ተጫነባት፡፡ ጣሪያ ላይ ተወልዳ ጣሪያ ላይ አደገች፡፡ ሰውን ደግሞ እናውቀዋለን፤ የእኔ ነው ብሎ ካላሰበ እንኳን እንስሳ የገዛ ወገኑንም አያበላም፡፡”
ስብሐት ለእራሱ ከተቆረጠለት መቁነን ላይ ድመቷን ማጋራት ጀምሮ ነበር፡፡ እንደውም አንዳንድ ቀን ሁሉንም ለእሷ ሰጥቶ ጦሙን የሚውልበት ጊዜ አለ፡፡
“አንተስ?” ሲባል
“እኔ ለምኜ ሳይሆን ተለምኜም የሚያበላኝ አላጣም” ይላል፡፡
ድመቷን የሚመግብበት ሥርዓት ጥንቃቄ የተሞላበት ነበር፡፡ ቁርሱን ወይ ምሳውን ይዞ ከቤቱ ይወጣና ድመቷን በአይኑ ሳያፈላልግ መኖሪያዋ የሆነው ወሻቃ ቦታ አካባቢ ያስቀምጠዋል። ከዚያ ቀጥ ብሎ ወደ ክፍሉ ገብቶ ማንበብ ይጀምራል። ከተወሰነ ቆይታ በኋላ ቀስ ብሎ ምግቡን ወዳስቀመጠበት አቅጣጫ ገልመጥ ይላል፡፡ ከበላች ሰሐኑን ያነሳል። ካልበላች ሌላ ጥቂት ጊዜ ይጠብቃታል፡፡ ሰዎች አብረውት ካሉ ፀጥ ብለው መፅሐፍ ወይም ሌላ ነገር እንዲያነቡ ያዝዛል፡፡ ከበላች፡-
“አርበኛችን ከእነኩራታቸው ተመግበዋልና አሁን ጨዋታ እንቀጠል” ይላል፡፡
አንድ ጊዜ እያሳለው ስለተቸገረ ዜና፣ ሞርቶዴላ እንዲበላ አቀረበችለት፡፡
“እቺን የያዝናትን አጠናቀን እንመገባለን” ብሎ ወደ ክፍሏ ከሸኛት በኋላ፣ እንዳለ ለድመቷ አቀረበላት፡፡
“ለምን?” አልኩት
“እውነታውን ሳንሸፍጥ ለመቀበል ከደፈርን ሞርቶዴላው የሚያስፈልጋት ለአርበኛዋ ነው። እንደውም አማልክቱ እንዲያስለን ፈቃዳቸው የሆነው ለእሷ በማሰብ ሳይሆን አይቀርም እንላለን፤ ባይመረመሩም፡፡ አሁን ፀጥታ ያስፈልጋል፣ አርበኛዋ ያለመሳቀቅ እንዲመገቡ፡፡”
በዚያ ዘመን መለወጫ እለት ወደ መካኒሳ ስሄድ የስብሐትና የድመቷ ግንኙነት ተሻሽሎ ተመለከትኩ፡፡ ስብሐት ለበአል የተሰጠውን ዶሮ ወጥ ከእነቅልጥሙ ለድመቷ አቅርቦ በረንዳ ላይ ያነባል፡፡ ድመቷ የእኔን መምጣት እስክትመለከት ድረስ ከጀርባው በመጠኑ ራቅ ያለውን ምግብ እየበላች ነበር፡፡ ተአምር የሆነብኝ፣ ስብሐት ወደ ክፍሉ ሳይገባ መብላቷ ብቻ ሳይሆን የሰውነቷ መለወጥ ጭምር ነው፡፡ ልጥልጥ ብላ ባትወፍርም መጠነኛ ሁኔታ ውስጥ መገኘቷ በራሱ ተአምር ሆኖብኛል፡፡ እኔን ስታይ ቱር ብላ ጠፋች፡፡
ስብሐት ቀልቡ ከእሷ ጋር እንደነበር በሚያስታውቅ ሁኔታ ቀና ብሎ አየኝ፡፡
“ለመደች?” ስል ጠየኩት
“በጥቂቱ”
“እንዴት?”
“አርበኝነታቸውን ባለመጋፋት፣ ከነፃነታቸው ምንም ጉዳይ እንደሌለን፣ ግዴለሽነትን እየተወንን፣ ተመግበው እንዲሄዱ እየፈቀድን… ወዘተ” አለ፡፡
ስብሐት ይቺን ድመት የሚያበላት እሩህሩኋ ብቻ አልነበረም፡፡ ረሃቧን የተካፈላት፣ አንዳንዴም ፋንታዋን የተራበላት ወዳጇ እንጂ፡፡
አፉን እየተመተመ ወደ አሱ ክፍል እንድገባ ጋበዘኝ፡፡ ሹክክ ብዬ አለፍኩ፡፡ ለጥቂት ደቂቃ መፅሔትና ጋዜጣ አገላበጥኩ፡፡ እሱ በረሃብ ጭምር የታደጋትን ድመት እኔ በፀጥታ ለማገዝ መሞከሬ እንደከበደኝ ታውቆኝ እራሴን ታዘብኩት፡፡
“አሁን መቀጠል እንችላለን” አለኝ፡፡
በራሴ ላይ አኩርፎ መቀጠል ተሳነኝ መሰል፡-
“ነፃነት የሚያስከፍለው ዋጋ ባሪያ በመሆንህ ከሚደርስብህ መከራ ጋር መነፃፀሩ የሰዎች እጣ ፈንታ ብቻ አለመሆኑን በዚች ድመት አውቀናል፡፡ አለማወቋ በጀ እንጂ፣ ብታውቅም ጉራ መንፋቱን ናቀችው እንጂ ወይም ስለ ነፃነት ከማውራት ነፃነቷን መኖር መረጠች እንጂ… አሜሪካኖችን ባስናቀች ነበር፡፡”
ወገቡን ይዞ ተነስቶ ቆመ፡፡ ብዙ ሲቀመጥ የሚያደርገው ሰውነት ማፍታቻ ስልቱ ነው፡፡ ወገቡን እንደያዘ ወደ ውስጥ እያየ ንግግሩን ቀጠለ፡፡
“የተወዳጃችን የማርክ ትዌይን እናት፤ በዚያ የሰዎች ገበያ ሥርዓት በተደናበረበትና የኑሮ ስልቱ በተወለጋገደበት ዘመን፤ (Great depression) የድመቶች ከየቤቱ መባረር ሐዘን ስለፈጠረባቸው እየሰበሰቡ ሰላሳ ያህሉን ማስጠጋት ችለው አስደንቀዋል፡፡ ያውም ከልጃቸው ጀምሮ የሚደርስባቸውን ተቃውሞ ተቋቁመው፡፡ ሌላው አንድ ድመት ከብዶት እኮ ነበር ወደ ጐዳና የሚያባርረው፤ እንኳን ሰላሳ አንዲቷ እንዴት እንዳሽቆጠቆጠችን በማሰብ መንፈሳቸው በሰላም እንዲያርፍ እንመኛለን፡፡”
ከሦስት ወር በኋላ ይመስለኛል፤ ተመልሼ ስሄድ ድመቷ ስብሐት ክፍል ድረስ መጥታ የመጮህ ወግ ደርሷት አየሁ፡፡
ምንም እንኳን እኔን ስታይ በርግጋ ብትጠፋም ሰውነቷ፣ ፍጥነቷና ንቃቷ በደንብ የተያዘች የቤት ድመት አስመስሏታል፡፡ ገረመኝ፡፡
“ያቺ ድመት ነች?” ባለማመን ጠየቅሁት
“እ…” አለኝ፡፡ “ነፃነቷን ጨርሳ ባለመተው፣ መጠነኛ ድጋፋችንን በመሻት፣ ፈር ያልለቀቀ ጥያቄዎችን ታቀርብልናለች፡፡ ደግሞም’ኮ እውነቷን እንደሆነ ተቀብለንላታል፡፡ የተፈጥሮ ባርነት መች አነሳትና የሰዎችን ትደርብ? እራሳቸው የተፈጥሮ ባሮች እንደሆኑ አጣነውና? ድንቄም ጌታ! ልትለን ትችል ነበር ያውም በመፀየፍ፡፡ አድርባይ ምሁሮች ስለበርን ለማዳ ድመትነትን ከእነጭራ አቆላሏ አጥርተን ስለምናውቅ ለአርበኛችን አንመኝላቸውም - ምን ቦጣቸውና…”
ከሁለት ወይም ከሦስት ወር በኋላ ስብሐት ያንን ቤት ለቀቀ፡፡ የነፃነት አርበኝቷ ያለስብሐት፣ ኑሮ እንዴት ተገፍቶላት ይሆን? ለብዙ ዘመን አብሮኝ የኖረ ጥያቄ፡፡

Published in ህብረተሰብ
Friday, 13 September 2013 12:38

ሆደ ሰፊው ባሕር

ሆደ ሰፊው ባሕር
የአዲስ ዓመት ንጋት
የአዲስ ዓመት ጠዋት
ምን ያሳየኝ ይሆን?
እያልኩኝ ስጠይቅ፣ በማለዳ ጉጉት፤
የመጣውን ዘመን፣ ወንዝ ሆኖ አገኘሁት፡፡
የመስከረም ፀሐይ፣ የአደዬ ጅረት ነው
የመስከረም ፀሐይ፣ የአበባ ወንዝ ነው
የአበባ ፍቅር ጽንፍ፣
አሊያም የመንፈስ ጐርፍ፤
በራሪው ጊዜ ነው፣ ክንፉ እማይታጠፍ፡፡
ወንዝ ሆኖ አገኘሁት፣ የ’ስካሁኑን ዘመን
ስንት ዓመት የኖረ፣ የዕድሜ አበባ - ጉንጉን
የባሕሩ እርጋታ …አሁን ያገኘነው፣
ከብዙ ርኩቻ፣ ኋላ ነው የመጣው፡፡
ጠብታ ከሰማይ ምድር ተጠራቅማ
ወንዝ ሆና፣ ጐርፍ ሆና- ስታንቀሳቅሰው
ያን የክረምት አጀብ ያን የውሃ ጀማ
አንድ አገር አክላ
ከባህሩ ስትገባ፤
መናገሯ ነ በውሃ ልሣኗ፣ በውሃ ትረካ
እያደር ማደጉን፣
ቀንም ወደዘመን፣ችግኝ ወደ ዋርካ፡፡
አንዱ ውሃ ሌላውን ሲያባርረው ውሎ
ሂያጅም ሆነ ኗሪ
ክፉም ሆነ በጐ፤ ሰብቶም ሆነ ሰልሎ
ማረፊያው ባህር ነው፤ ሞቶም ሆነ ገሎ
“እስኪ ተመልከተው ይህ አወራረድ
ያልሰማው ሲመጣ የሰማው ሲሄድ”
የተባለለት ወንዝ የውሃው ሙላት
ባሕሩ ውስጥ ያርፋል ቀን የሞላ ለት፡፡
ዘመን ይለወጣል በወንዙ ፍሰት፡፡
ሆደ ሰፊው ባሕር ስንቱን አስተናግዷል
ያገር እኩያ ነው ዛሬም ገና ያድጋል፡፡
ጊዜም ፈስሶ ፈስሶ፣ ከወንዞቹ ጋራ
ባሕሩ ላይ ይከትማል፣ የውሃው ደመራ፡፡
ሆደ ሰፊው ባህር፣ ሁሉን አቻቻይ ነው
የኢትዮጵያ ምልክት፣ የዘመን ባሕር ነው!
ስንቱን ደራሽ ውሃ
ስንቱን ውሃ ሙላት
ስንቱን ዱታው ዘራፍ
ስንቱን የድንገት ጐርፍ፤
ቁጣውን አብርዶ
እንደምድር ችሎ
እንደልጅ አባብሎ፤
ገላው ያረገዋል፣ ስሙን ባሕር ብሎ!!
ሆደ - ሰፊው ባሕር፣ የውሃ እልፍኝ ነው
ሆደ - ሰፊው ባሕር፣ የውሃ ሸንጐ ነው
ሆደ - ሰፊው ባህር የኢትዮጵያ እኩያ ነው፡፡
ማዕበል ንፋሱ፣ ውሃውን ይገፋል
ሶምሶማው ሲረግብ፣ ባህሩ ዳር ያበቃል፡፡
ጐርፉም ጐርፎ ጐርፎ፣ ባህሩ ውስጥ ይተኛል
ባሕሩ ሆደ - ሰፊው፣ ስንቱን አስተናግዷል
የኢትዮጵያ ሙቀት ነው፣ ዘመን ይለውጣል፡፡
ከማዕበል በፊት የባህሩ እርጋታ
የዓለምን ሁለት ፊት፣ ተፃራሪ ፋታ
ያሳያል ያን ዳገት፤ ያሳያል ቁልቁለት
ያሳያል አፋክሮ፣ ያሳያል አፋቅሮ፣
ያሳያል አካሮ፤
ተለዋዋጩን ገጽ አጥንቶና አጥቁሮ
የዘመኑን ልደት ዛሬም ዳግም ቆጥሮ!
የባሕሩ ቀን ሆኗል፣ የዓመታት ጅማሮ!!
የባሕሩ ቀን ሆኗል፤ የአበቅቴ ቋጠሮ፡፡
ጳጉሜ 1 2006 ዓ.ም
(ለእንቁጣጣሽ 2006 እና ለ25ኛው)

Published in የግጥም ጥግ
Friday, 13 September 2013 12:37

የዕንቁጣጣሽ ስጦታ

አበው ሲሉ ሰማሁ፤
“እኔ እበልጥ እኔ እበልጥ፣
ፉክክር ምንድን ነው
ዕድል በትከሻ፣ ሙያ በልብ ነው”
እኔም ዛሬ ቀጠልኩ፤
ውጣ ውረድ በዝቶ፣
ልብ ያረጀባችሁ
በዚህ እንቁጣጣሽ፣ አዲስ ልብ ይስጣችሁ!
ጳጉሜ 4/1997 ዓ.ም
ነ.መ

 

===============

መልካም አዲስ አመት ይሁንላችሁ!
በአሉ:-
ጐረቤት የተገዛ በግ ወይም ዶሮ Like የምናደርግበት፣ አይተንም Comment የምንሰጥበት ብሎም በግ ወይም ዶሮ ሲሰራ አሽትተን TAG የምናደርግበት እንዲሁም ጐረቤት በግ መግዛቱን ላላዩ ወይም ላልሰሙ ሰዎች Share የምናደርግበት በዓል ይሁንልን፡፡
ፌስ ቡክ ለዘለዓለም ትኑር!!
(ከፌስ ቡክ የተገኘ)

Published in የግጥም ጥግ

አምላኬ ሆይ!
በዚህ አዲስ ዓመት
ምነው ያንዷን ድምጿን
ምነው ያንዷን ሳቋን
ምነው ያንዷን ሽንጧን
ምነው ያንዷን ባቷን
ምነው ያንዷን ጡቷን
ምነው ያንዷን ዓመል
ምነው ያንዷን አንጐል
ያንዷን ጨዋታዋን
የሚጥም ለዛዋን
ከየአካሏ ነጥቀህ
ከገላዋ ሰርቀህ
ሁሉን ማግኘት ብችል ነጥዬ ለብቻ
ሙሉ ሴት ለማግባት፣ አዋህዶ አንድ አርጐ፣ የህይወትን አቻ
ይሄ ነው ፀሎቴ
ንጥሩ ምኞቴ
በሌት - ቀን ጐዳና
እንዲህ ነው እምወድ ‘ራሴን በጠና!
ያው እንደምታውቀው፤
ራስ ወዳድነት
ሌላውን ካልነካ፣ ምን ክፋት አለበት?!
አሜን…አሜን…አሜን…ለወንደላጤነት፡፡
ለዚህ ነው እስካሁን ሚስት ያላገባሁት፡፡
አምላክ ሆይ አድምጠኝ፡፡
ወይ ማረኝ፤
ወይ ዳረኝ፡፡
ወይ እኔኑ አጽድቀኝ፣ ወይ ምርጫዬን ስጠኝ!
አምላክም መለሰ፡-
አዳም ወንደላጤው ስማ መስሚያ ካለህ
ከግራ ጐንህ ላይ፣ አንድ ያጐደልኩብህ
ሙሉ እንደማትሆን፣ ነበረ ልንገርህ፡፡
ስንት ዘመን ኖረህ፣ አሁንም አልገባህ፡፡
ምኞት ብቻኮ ነው፣ ፍፁምነት ማለት
ይህ ገብቶህ አግባና፣ ያቅምህን አንዲት ሴት
ተዳምራችሁ ሙሉ፣ ይሄን ያንተን ፀሎት
አለዛ እርግማኔ
በብቸኝነት እጅ፣ በቅን ፍቅር ጠኔ
ስትመርጥ እንድትኖር ነው፣ ያላንዳች ውሳኔ፡፡
ኩነኔ ማለት ነው፣ የወላዋይ ወኔ!!
ማነብነቡን ተወው፣ አይጠቅምህም ፀሎት
ይልቅ ዝቅ ብለህ፣ እጅህን ዘርጋላት
የህይወት እኩያህ፣ እንድትመጣ አንዲት ሴት
ሂጂም አትበላት፣ ነይም አትበላት
የእንቁጣጣሿ’ለት፣ አበባ አዙርላት!
ሰኔ 1998 ተጀመረ ሰኔ 2005 አለቀ)
(ለብኩን ወንደላጤ)

Published in የግጥም ጥግ
Friday, 13 September 2013 12:35

ሳያልፍብን ውዴ...

ዘመን ሳይለወጥ እቴ ውዴ ሆይ
መግደርደር ተይና አንዴ እንተያይ!
ዝናቡን ዘንግተሽ፤ ጳጉሜን ግን አስታውሰሽ
ዣንጥላ ሳትይዢ በታክሲም ሳትመጪ
እንጠመቅ ፍቅር ከዝናብ ጋር ውጪ፡፡
ወደ አውላላ ሜዳ ተሸክሜሽ ልክነፍ
ያንቺ ጉልበት እስኪያልቅ
የኔ እስኪንጠፈጠፍ፤
ወድቀን እንጫወት
ፍቅር ለጭቃ አይሰንፍ!
ከዚያም እንተኛ ትራስ ሆኖሽ ክንዴ
የጭቃ ላይ ፍቅር ውብም አደል እንዴ?
እንደተጋደምን እንደተዋሃድን
ለፍቅራችን ማህተም ትሆንልን ዘንዳ፤
ፍቀጅላት ውዴ - መስከረም አንድ ሲል
ከናፍራችን ላይ
አደይዋ ትፈንዳ!
ለዑል ብርሃኑ
ነሐሴ 26/97

Published in የግጥም ጥግ
Friday, 13 September 2013 12:35

ጭፈራችን ተመልሷል!

“ጭፈራችንን መልሱ”፤ ብለን ነበር ትላንት በስቲያ
“አገራችንን መልሱ”፤ ብለን ነበር ትላንት በስቲያ
የሰሙን ምሥጋን ይግባቸው፤ እሰየው አለች ኢቶ’ጵያ!!
ወትሮም መደማመጥ እንጂ፣ መደነቋቆር ክሶ አያቅ
ቆርጠው ካልበጠሱት በቀር፣ ከዘመዘሙት ቂም አያልቅ
ዛሬን ድል አገኘሁ ብሎ፣ የነግ ፈተናም አይናቅ!

በአገር ጉዳይ ቂም አያቅም፣ ይሄው ህዝቡ ይጨፍራል፡፡
ይሄው መሬቱ ይጨሳል፡፡
ባንዲራው እንደነበልባል፣ ዳር ከዳር ይንቀለቀላል!!
መብራት ቢጠፋ ምን ግዱ፣ ህዝቡ እሳት ሆኖ ይበራል
ብርሃን ነው ይነድዳል አበሽ፤ ኤሌትሪክ ነው ይያያዛል!!
ዕድሜ ለልጆቻችን ጭፈራችን ተመልሷል፡፡
“…እስኪበጣጠስ ላንቃችን”
መጅ እስኪያወጣ ጉሮሮአችን
“አገር ላዕላይ ነው” እንዳልን
እንደህፀፁ ብዛት ሳይሆን፣ እንደልባችን ጽናት
አቆጥቁጦ ልሣናችን፣ እስከነገና እስከትላንት
እንደፊኒክስ ከረመጥ፣ ከትቢያ እንነሳለን፡፡
እንደ ድመት ዕድሜ ጥናት አሥራ ሶስት ነብስ ነው ያለን፤

ከሣግ ጩኸት ሞታችን ውስጥ፣ ለእንቁጣጣሽ ፀሐይ በቃን!
ህይወትም ትግል ነውና፣ መከራችንም ባያልቅ
ይውለበለባል እንጂ፣ ባንዲራ አያዘቀዝቅ
ልብ ነብሱን ይገብራል፣ ጀግና አገሩ እስከምትስቅ
ዕድሜ ለልጆቻችን እግራቸው ላልዶለዶመ
ያም ያን ቢል፣ ያም ያን ቢላቸው፣ ቅን ቅስማቸው ላልታመመ፡፡
ወትሮም አቀርቅረው እንጂ፣ አንዴ ከተለኮሱማ
የወይራ ለበቅ ናቸው፣ የቁርጡ ቀን ከመጣማ
በአሸዋ እርሻም ሜዳ ቢሆን፣ አንዴ አውድማ ከገቡማ
መንሽ ነው ልባም እግራቸው፣ አሂዶ እኮ ነው ኳሱማ!!
ምሥጋና ይግባቸው አቦ!!
ዕድሜ ለልጆቻችን
ተመልሷል ጭፈራችን!!
አካፋን አካፋ እንዳልነው
ወርቅ እግሩን እናመስግነው፡፡
ይህንን ባህል እናርገው፡፡
ዛሬስ ህዝባችን ታድሏል
የእንቁጣጣሽ ድል አዝምሯል!
የሀገር ፍቅር ነው እንጂ፣ ወኔ ወጌሻ አይፈልግም
ወድቆ መነሳትን ማወቅ፣ ልብ እንጂ ወግ አይክሰውም
ሐሞትን አጠንፍፎ እንጂ፣ በዕንባ ጐርፍ ጉድፍ አይጠራም፤
በቆራጥነት በተቀር፣ የልባም ቀን ጥም - አይቆርጥም፡፡
ጨክነው ከተዘጋጁ፤ እንዲህ እዚህ ይደረሳል
ህዝብም አካሉን ሁሉ፣ በባንዲራ ይነቀሳል…
የአገሩን ቀለም ይኳላል
አገሩን ፊቱን ይቀባል፡፡
በቄጤማ በዐደይ ማህል፣ ኳስም ጮቤ ረገጠች
ኳስም አበባ - አየሁ አለች
የነግ መንገዷን ለማብራት፣ የተስፋ ችቦ ለኮሰች
“የሽንፈት ምንቸት ውጣ”፣ “የድሉ ምንቸት ግባ” አለች!!
ዕድሜ ለልጆቻችን፣ ተክሷል ህዝብ ተክሷል
የአዲሱን ዓመት፣ ድል ለብሷል
በደልም በድል ይረሳል፤
ድል በትግል ይወረሳል!!
ጭፈራችን ተመልሷል!
ጳጉሜ 2 2005 ዓ.ም
(ዛሬም ለኳስ ተጨዋቾቻችንና
ለቅኑ የኢትዮጵያ ህዝብ)

Published in የግጥም ጥግ

አምባሳደር ዲና ሙፍቲ (የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ)

“የዓመቱ ትልቁ ፈተና የጐረቤት አገሮችን ሰላም ማስፈን ነበር”

በአጠቃላይ እንደ አገር በ2005 በርካታ ስራዎች ተሰርተዋል፡፡ በዋናነት በድህነት ቅነሳ ላይ ነው ያተኮርነው፡፡ ትልቁ የዘመናት ችግራችን ድህነት በመሆኑ እሱን ለመቀነስ የተደረጉ እንቅስቃሴዎች ከሞላ ጐደል ቢሆንም ውጤታማ ነበሩ፡፡ ሌላው የመልካም አስተዳደር ጉዳይ ላይ የተጀመሩ ስራዎች ሲሆኑ በዚህ ረገድም ስኬታማ ስራዎችን ሰርተናል፡፡ ግን ብዙ ርቀት ይቀረናል፡፡ ሰላምን በመላው ኢትዮጵያ ማስፈን ሌላው ስራችን ነበር፡፡ ዴሞክራሲያዊ ስርዓትን ለማስፈንም ሆነ ድህነትን ለመቀነስ ሰላም መስፈን አለበት፡፡ መንግስት በውጭም በውስጥም የሚሰራቸው ስራዎች አሉ፡፡ በተለይ በውጭ ጉዳይ ደረጃ የትራንስፎርሜሽን እቅዱን ለማሳካት ከውጭ በንግድ ዘርፍ፣ በቴክኖሎጂ ዝውውር፣ በኢንቨስትመንት፣ በቱሪዝምና መሰል ጉዳዮች ፋይናንስን ለመሳብ በርካታ ጥረቶች ተደርገዋል፡፡ ነገር ግን አሁን ካሉብን ችግሮች አንፃር፣ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ድህነትን ለመቅረፍና አገሪቱን መካከለኛ ገቢ ካላቸው አገሮች ተርታ ለማሰለፍ ከፍተኛ ጥረቶች መደረግ ይኖርባቸዋል፡፡ በግሌም ከነዚህ ጋር የተሳሰሩ ስራዎች ላይ ተሳትፌአለሁ፡፡ አጠቃላይ አመቱ ጥሩ ነበር፡፡
በ2005 ዓ.ም እንደፈተና የምናነሳው ከበፊት አመታት ተዛውሮ የመጣው የጐረቤት አገሮችን ሰላም የማረጋጋት ስራ ነበር፡፡ በሶማሊያ አዲስ መንግስት የመመስረትና አዲሱን መንግስትም የማረጋጋት እንዲሁም፣ የአካባቢው ችግር የሆነውን አል-ሸባብ የማስወገድና ሁለገብ ሰላምን የማስፈን ጉዳይ ትልቁ ፈተናች ነበር፡፡
ሆኖም ይህን ፈተና በብቃት የተወጣነው ይመስለኛል፡፡ ሌላው በሁለቱ ሱዳኖች መካከል ሪፈረንደሙ (ህዝበ-ውሳኔው) በሰላም እንዲሳካ ማድረጋችን ነው፡፡ ይሁን እንጂ ድህረ-ሪፈረንደሙ ከሀብት ክፍፍል፣ ከህግ ጉዳዮችና ከጐረቤት አገሮች ጋር ተያይዞ ከበድ ያሉ ነገሮች ነበሩት፡፡ ይህንንም በጥሩ ሁኔታ ተወጥተነዋል ብዬ አምናለሁ፡፡ በአጠቃላይ በውጭ ግንኙነት ትልቅ ትኩረትና ጥረት የጠየቀው የጐረቤት አገሮችን ሰላም ማስፈን ነበር፡፡ ምክንያቱም የጐረቤት አገሮች ሰላም የእኛም ሰላም ነው፡፡ የእነሱ ልማት የእኛ ልማት ነው። የእነሱ መረጋጋትም እንዲሁ የእኛ መረጋጋት ነው፡፡ እሱም ቢሆን በስኬት ተጠናቅቋል፡፡ ገና መጠናከር የሚገባቸውና ሊስተካከሉ የሚችሉ ግንኙነቶች ይኖራሉ፤ እነሱም በሂደት ይሳካሉ ብለን እናምናለን። በ2006 የበለጠ ብዙ ነገሮች ይስተካከላሉ፡፡ በ2006 በአለም ዙሪያ ከጋራ ጥቅማችን ጋር በተያያዘ አለም አቀፍ ህግና ስርዓትን በጠበቀ ሁኔታ ግንኙነታችን ማጠናከር ትልቁ እቅዳችን ነው፡፡ ለእናንተም ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብም መልካም አዲስ አመት እንዲሆን እመኛለሁ፡፡ አመሰግናለሁ፡፡

============
“የኢህአዴግ አምባገነንነት ተጠናክሯል”
ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ (“የአንድነት” ፓርቲ ሊቀመንበር)
በ2005 ዓ.ም ስብሠባዎችና ሠላማዊ ሠልፎችን ለማካሔድ ከመንግስት ፍቃድ የመጠበቅ አዝማሚያ ታይቷል፡፡ ይሔ ግን ትክክል አልነበረም። ስብሠባዎችንና ሠላማዊ ሠልፎችን ለማካሔድ የሚያስፈልገው ፍቃድ መጠየቅ ሳይሆን ማሳወቅ ብቻ ነው፡፡ በህገ መንግስቱ ላይም ሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባ ማሳወቅ እንጂ ማስፈቀድ ያስፈልጋል አይልም፡፡ መንግስትም እውቅና መስጠት ነው እንጂ የመከልከል መብት እንደሌለው ህጉ ይገልፃል። አሁን አሁን በፖለቲካ ድርጅቶች በኩል ይሔ ግንዛቤ ተፈጥሮ በህገመንግስቱ መሠረት በማሳወቅ (እውቅና ቢያገኙም ባያገኙም) ህዝባዊ ስብሰባና ሰልፎች ማካሄድ ጀምረዋል፡፡ በፓርቲዎች ውይይት የግንዛቤ ማስጨበጫዎች ተሰጥተዋል፡፡ ሠማያዊ ፓርቲ ሠላማዊ ሠልፍ አድርጓል፡፡ ያንን ተከትሎም አንድነት፤ በርካታ ሠላማዊ ሠልፎችና ስብሠባዎች አካሒዷል። ስለዚህ ተግባራዊ የሠላማዊ ትግል እንቅስቃሴ ተጀምሯል ማለት ይቻላል፡፡ የህዝቡ ችግር አፍንጫው ላይ ደርሷል። ይህንም ችግር በህዝባዊ ስብሠባዎች እና ሠላማዊ ሠልፎች ላይ እያንፀባረቀ ነው፡፡ ከ2004 ዓ.ም የተለየ ለውጥ ያየሁት ይሄ ነው፡፡ ኢህአዴግ ላይ ደግሞ አምባገነንነቱ እየጨመረ መምጣቱን አይቻለሁ። በ2005 ዓ.ም የተካሔደው ምርጫም ኢህአዴግ አምባገነንነቱን ምን ያህል እንዳጠናከረ የሚያሳይ ነው፡፡ 2006 ዓ.ም እነዚህ ችግሮች ተቀርፈው የምናይበት እንዲሆን እመኛለሁ፡፡ ያለዚያ ህዝቡ ኢህአዴግ ላይ ተነስቶ ችግር እንዳይፈጠር ስጋት አለኝ፡፡ ስለዚህ ኢህአዴግ ያጠበበውን እና የዘጋውን የፖለቲካ ምህዳር እንዲያሰፋና እንዲከፍት ነው የምጠይቀው፡፡ ህዝቡም የተጠናከረ ትግል የሚያደርግበት፣ መብቱን የሚያስከብርበትና ለነፃነቱ የሚታገልበት ዓመት እንዲሆን እመኛለሁ፡፡

===========

“ኢህአዴግ ራሱን መፈተሽ አለበት”

አቶ ሙሼ ሰሙ (የኢዴፓ ሊቀመንበር)
በ2005 ዓ.ም በፖለቲካው የተሻሻለ ጉልህ ነገር አላየሁም፡፡ አመቱ መገባደጃ ላይ በውንጀላ የታጀቡ ሠላማዊ ሠልፎች ቢካሄዱም ያንን እንደ ፖለቲካ ለውጥ አላየውም፡፡ ከዚህ ቀደም በነበሩ ምርጫዎች ለፖለቲከኞች የአየር ሠአት ይሰጥ ነበር፤ ዘንድሮ ግን አልተሠጠም፡፡ ለምርጫ ቅሰቀሳ የሚያስፈልጉ ቁሳቁሶች ለመስጠትም መንግስት ፍቃደኛ አልነበረም። ከሁሉም እጅግ አሳዛኙ ነገር በተቃዋሚ ፓርቲዎች እንቅስቃሴ ላይ ብዙ ችግሮች መድረሳቸው ነው፡፡ መታሠር፣ መደብደብ፣ የመሳሰሉ፡፡ ችግሮቹን ማጣራት ሊያስፈልግ ይችላል፡፡ ነገር ግን እሮሮ ዝም ብሎ ከመሬት ተነስቶ አይመጣም፤ ደረጃውን መለየት ቢያቅተኝም፡፡
ነፃ ፕሬሱም ያለ ጭንቀትና ያለ ውጥረት መስራት የሚችልበት ሁኔታ መፈጠር አለበት እላለሁ፡፡ ከዚህ አንፃር ኢህአዴግ ቆም ብሎ ራሱን መፈተሽ አለበት፡፡ ዲሞክራሲ እያደገና እየጐለበተ መምጣት ያለበት ነገር ነው፡፡
በሠነድ ላይ ብቻ መስፈሩ በቂ ነው ማለት አይቻልም፡፡ በተግባር መታየት አለበት፡፡ ኢህአዴግ ዲሞክራሲያዊ መብቶችን የሚያስከብሩ ህጐችን አውጥቻለሁ ሊል ይችላል፡፡ ግን እነዛን ህጐች በሌላ ህግ በመሻር እንደሽብር ህጉ መብትን ሲነፍግ ደግሞ አይተናል፡፡
ስለዚህ እነዚህ ነገሮች ተወግደው አዲሱን አመት በአዲስ ለውጥ እንደምሳናልፈው ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

============

“አዲሱን ዓመት በስጋትና በተስፋ እንጠብቀዋለን”
አቶ አስራት ጣሴ (የ“አንድነት” ፓርቲ ዋና ፀሃፊ)

በ2005 ዓ.ም የገዢው ፓርቲ የሠብአዊ መብት ጥሠት በከፍተኛ ደረጃ ጨምሯል፡፡ ከፖለቲካ ምህዳሩ መጥበብ አንፃር ከፍተኛ ወከባና ማስፈራራት ደርሷል፡፡
የዲሞክራሲያዊ መብት ነጠቃው አይሏል። ከምንጊዜውም በላይ የኢትዮጵያን ህዝብን መብት ያለአግባብ ለመጨፍለቅ በማን አለብኝነትና በአምባገነንነት የፈለገውን ሲያከናውን ታይቷል። ሁለንተናዊ የሆነ ጭቆናና በደል በህዝቡ ላይ ተፈፅሟል። “አንድነት” ፓርቲም ሆነ 33ቱ ፓርቲዎች የህዝቡን ችግሮች ለመፍታት ከፍተኛ እንቅስቃሴዎችን እያደረግን ያሳለፍንበት ዓመት ነው፡፡ ህዝቡም ትጥቁን አጠናክሮ ለሠላማዊ ትግል የተነሳሳበት ጊዜ ነበር፡፡ የህዝቡ ጥያቄዎች በአደባባይ በግልፅ ቀርበው ከመንግስት ጋር የተፋጠጡበት ሁኔታ ታይቷል፡፡ በ2006 ዓ.ም የታሰሩ ፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች እንዲሁም የሃይማኖት መብት ጥያቄ በማንሳታቸው ወህኒ የገቡ ግለሰቦች የህግ የበላይነት ተረጋገጦ እንዲለቀቁ እመኛለሁ፡፡ “በእኔ ጎዳና ከተጓዝክ በአውራ ጎዳናው ተጓዝ፤ አለበለዚያ ግን አትጓዝም” የሚለው የአምባገነኖች አይነት አካሄድ እንዲቆም እመኛለሁ፡፡ አዲሱን ዓመት በስጋትና በተስፋ የምንጠብቀው ቢሆንም ኢትዮጵያን ፈጣሪ ይባርካት፡፡ ሰላም የሰፈነባትና የዜጎቿ ጥያቄ በአስቸኳይ የሚመለስባት አገር ትሁን፡፡

===========

“በህዝብ በኩል መነቃቃት ተፈጥሯል”
ኢ/ር ይልቃል ጌትነት (የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር)
በ2005 ዓ.ም የታዩት ለውጦች በሦስት መንገድ ማስቀመጥ ይቻላል፡፡ ለውጥ በመንግስት በኩልና ለውጥ በተቃዋሚዎች በኩል፡፡ ለውጥ በህዝቡ በኩል በኢህአዴግ በኩል ወደ ኋላም ወደ ፊትም ለመሔድ ፈራ ተባ እያለ፣ ቆራጥ የፖለቲካ ውሳኔ መስጠት ባለመቻሉ እጁ ላይ ያሉ ችግሮች ከዕለት እለት እየተባባሱ ሄደዋል፡፡ ለምሳሌ የእስልምና ዕምነት ተከታዮችን በተመለከተ የተፈጠረው ችግር ይጠቀሳል፡፡ በሚዲያው ላይ የደረሰው አፈናና አስተዳደራዊ በደል ሚዲያዎችን ከጨዋታው አስወጥቷቸዋል፡፡ በማህበራዊ ጉዳይም ቢታይ የኑሮ ውድነቱ፣ ሙስናው፣ የትራንስፖርት ችግሩ፣ የመብራት፣ የውሃና ሌሎች ችግሮች ፍፁም ባልተጠበቀ ሁኔታ ተባብሰው ህዝቡ በኢህአዴግ ላይ ያለውን እምነት እንዲያጣ አድርጎታል፡፡ በኢህአዴግ በኩል ምንም መሻሻል አልታየም፡፡ በህዝቡ በኩል ግን መነቃቃት ተፈጥሯል፡፡ ጋዜጦችን የማንበብ ፍላጐት፣ በማህበራዊ ድረ ገፆች ላይ መሳተፍ፣ በድፍረት የመነጋገር፣ ፓርቲዎች በሚያቀርቧቸው መድረኮች ላይ የመገኘት ሁኔታዎች ታይተዋል። ትንሽም ቢሆን ተስፋ የማድረግና የመለወጥ አዝማሚያ አለ፡፡ ለውጥ የሚያመጣ አመራር ቢያገኝ ህዝቡ ለመለወጥ ዝግጁ ነው፡፡
ተቃዋሚዎችም ኢህአዴግ በሚያደርስብን በደል ከማለቃቀስ ተላቀን ችግሮችን በአደባባይ ከህዝብ ጋር መወያየት ጀምረናል፡፡ ይሄ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት፡፡ ፖለቲካ የሀገር ጉዳይ ነው፤ ኢህአዴግ የዚህን አገር ችግር በራሱ “ተዓምር” ሊፈታው አይችልም፡፡ ስለዚህ ተቃዋሚዎች፤ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ለመብታቸው እንዲቆሙ እና መብታቸውን ለማስከበር እንዲጥሩ የጀመሩትን እንቅስቃሴ አጠናክረው መቀጠል ይገባቸዋል፡፡ 2006 የመልካም ስራ፣ የፍቅርና የጓደኝነት ዘመን ይሁንልን፡፡


===========

“አፈናና ጭቆና የበዛበት ዓመት ነው”
አቶ አበባው መሳይ (የመኢአድ ሊቀመንበር)

በተጠናቀቀው ዓመት የተለወጠ ነገር አለ፡፡ ወደ መልካም ሳይሆን ወደ ባሰ ሁኔታ ነው የገባነው፡፡ እስር እና የተለያዩ ጭቆናዎች የበዛበት አመት ነበር። በእርግጥ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች በአንድነት ለመስራት ተንቀሳቅሰዋል፡፡
የኢህአዴግ መንግስት በህዝባችንም ሆነ በተቃዋሚ ፓርቲዎች ላይ ከፍተኛ አፈናና ጭቆና ያደረሠበት ዓመት ሆኖ አልፏል፡፡
ወደድንም ጠላንም ሁላችንም ኢትዮጵያኖች ነን፡፡ አገራችንን ወደ ሠላማዊ መንገድ ለማምጣት የገዢነት ሳይሆን የአመራር ስሜት ያስፈልጋል፡፡ ኢህአዴግ በ2006 ዓ.ም ህዝቡን አሳታፊ የሚያደርግ ሁኔታ በመፍጠር አገራችንን ወደ ጥፋት ከመምራት ይልቅ ወደ ሠላም ለማምጣት እንደሚሰራ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
ይሔንን ባያደርግ ግን ሁኔታዎች ወደ ከፋ ሁኔታ እንደሚሔዱ እገምታለሁ፡፡

“ከብረው ይቆዩኝ ከብረው
ባመት ወንድ ልጅ ወልደው!
አምሣ ጥገቶች አሥረው…!”
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አሳማ፤ በጐች በብዛት ወደተሰማሩበት የግጦሽ መስክ ጐራ ይላል፡፡ እረኛው “ምን ሊያደርግ መጣ” በሚል ጥርጣሬ ያስተውለዋል፡፡ አሳማው ወደ በጐቹ ለመቀላቀል ይሞክራል፡፡ እኛው ያደፍጥ ያደፍጥና ፈጥኖ ተጠግቶ አሳማውን ይይዘዋል፡፡ ከዚያም፤
“ለምን መጣህ?” ብሎ ይጠይቀዋል፡፡
አሳማውም፤
“ከበጐች ልመሳሰል ጀ.ቨ” ሲል ይመልሳል፡፡
“ተመሳስለህስ?”
“እንደበጐች ልኖር”
“ኖረህስ?”
“እንደበጐች እንድታኖረኝ!?”
“አንተን እንኳን ለዚህ አልፈልግህም አያ አሳማ”
“እንግዲያ እንዴት እንድኖር ትፈልጋለህ?”
“አይ፤ ኑሮው ይቅርብህና ወደገቢው ቦታ ብወስድህ ነው የሚሻለው፡፡” ብሎ፤ እየጐተተ ወደ እንስሳ ማረጃው ቦታ ይዞት ሊሄድ ይጐትተዋል፡፡
አሳማው፤ መወራጨት፣ መንፈራገጥ፣ ማጓራት መጮህ ይጀምራል፡፡
ይሄኔ ከበጐቹ መካከል አንዱ ብቅ ይልና፤
“አያ አሳማ?” አለ በለጋስ ጥያቄ ቅላፄ፡፡
“አቤት” አለ አያ አሳማ፡፡
“ምንድነው እንደዚህ የሚያስጮህህ? እኛ ሁላችንምኮ በጌታችን እየተጐተትን ወደሌላ ቦታ እንወሰዳለን፡፡”
“ነው፡፡ ግን የእኔ ይለያል” አለ አሳማ፡፡
“እንዴት?” አለ በጉ፡፡
“አይ አያ በግ የሁለታችን ለየቅል ነው!”
“እኮ እንዴት?”
“ጌታህ አንተን የሚፈልግህ ከቆዳህ ሱፍ ለመሥራት ነው፡፡ እኔን የሚፈልገኝ ግን ለሥጋዬ ነው - ጠብሶ ሊበላኝ”
አያ አሳማ፤ እንደፈራው እየተጐተተ ሄደ፡፡
* * *
በአዲሱ ዓመት ከእንዲህ ያለ ምርጫ ይሰውረን፡፡ ለጥብስ ይሁን ለሱፍ፣ ዞሮ ዞሮ መታረድ ላይቀር ምርጫውን በቅናት መልክ ከማሰብ ይሰውረን፡፡ አራጁንም መሆን ታራጁንም መሆን በፖለቲካ ሥርዓት ውስጥ አሰቃቂ ነው፡፡
“አውራ ዶሮ ጮኾ መንጋቱን ነገረኝ
ዛሬ ማታ ላርደው ቀጠሮ ነበረኝ”
እንዳለው አንዱ የእኛ ገጣሚ፤ የታራጅና አራጅ ምፀት የምንነጋገርበት እንዳይሆን አዲሱ ዓመት ልቡን ይስጠን፡፡
አዲሱን ዓመት የእኩልነት ያድርግልን!
ይገብር ካላችሁ ዝንጀሮም ይገብር
የንጉሥ አይደለም ወይ የሚጭረው ምድር”
የምንልበት ዘመን ይሁንልን!
እንደ ዱሮው ሳይሆን እንደዛሬው ተስፋችን፣ ምኞታችንና ርዕያችን አይሞትምና
“ከብረው ይቆዩኝ ከብረው
ባመት ወንድ ልጅ ወልደው
አምሣ ጥገቶች ወልደው…
በኳስ በድል ታጅበው…”
ስንባል ሞቅ የሚለን፣ ከጭንቅ የሚገላግለን የአዎንታዊነት ምርቃት እንዲሆንልን እንጽና፣ እንጽናና፡
በመጪው ዓመት በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን፤ “የኢትዮጵያ ሬዲዮ መብራት በመጥፋቱ ከሚሴ አካባቢ የሥርጭት ችግር ገጠመኝ፤ አለ” የሚል ዜና የሚያሰማበት ዓመት እንዳይሆን እንመኝ!!
የአቦ - ሰጡኝ ሳይሆን የትግል ዓመት እንዲሆንልን ልብና ልቡናውን ይስጠን!
የችግር ማውሪያ ሳይሆን የመፍትሔ መፈለጊያ ዘመን እንዲሆንልን አንጐሉን ይስጠን!
የመለያያ ሳይሆን የመዋሃጃ፣ የመተሳሰቢያ ዘመን እንዲሆን በጐ አመለካከቱን አያጨልምብን!
ዕድሜ የጊዜ ሳይሆን፤ የመጠንከር፣ አቅም - የመገንባት፣ እርምጃችንን የማትባት ይሆንልን ዘንድ እርዳታው አይለየን፡፡
ሽቅብ እየተመነደግን እንጂ ቁልቁል እያደግን እንዳንሄድ፣ ድላችንን አስተማማኝ ያድርግልን፡፡
ፀሐፊዎቹ እንዳሉን፤
“አንድ ግዙፍ የብርቱካን ዛፍ እናስብ፡፡ በስሎ የተንዠረገገ ብዙ ብርቱካን አለው፡፡ ወደታች፣ በሰው ቁመት ያሉትን ብርቱካኖች በብዛት ለቀምኳቸው፡፡ ከዚያ በላይ ያሉትን ለመቅጠፍ ቁመት አጠረኝ፡፡ ከዚህ አንፃር ሲታይ የብርቱካን እጥረት አለ ልል ነው፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ግን አንድ አዋቂ ሰው አንድ ቴክኖሎጂ ፈጠረ፤ መሰላል የሚባል፡፡
ወደ ማይደረሱት ብርቱካኖች መድረሻዬን አበጀልኝ፡፡ ችግሬ ተቃለለ፡፡ ቴክኖሎጂ ወደኃይል ምንጭ መዳረሻ/ ማግኛ ስርዓት ነው፡፡ ያኔ እጥረት ያልነውን ነገር፣ አሁን በሽ - በሽ፤ ነው ያሰኘናል፡፡ (“አበንዳንስ”፤ በፒተር ዲያማንዲስ እና ስቲቨን ኮትለር)
ስለ ዕጥረትና ስለ ዕጦት የምናስብበት ዓመት እንዳይሆን መሰላሉን የሚሰጠን አዋቂ ይዘዝልን፡፡
የኳስ ድል ይለምልም፡፡ ሩጫውም ይቅናን፡፡
የዕውነት ለውጡም ይቅናን፡፡ ኑሮም ይታደገን!
በጐ እንድንመኝ፣ በጐ እንድናገኝ፤ በጐ እጅ ይስጠን!
“አይቀጭ ትልማችን፣ አይራብ ህልማችን!
አይመት ሐሞታችን፣ አይቃዥ ርዕያችን!
አይንጠፍ ጓዳችን፣ አትምከን ላማችን!
አይክሳ ቀናችን፣ አይላም ጉልበታችን!!
ከሁሉም ከሁሉም አይጥፋ ሻማችን!”
ብለን የምንመኝበትን የህይወት ፀጋ አይንሳን!!
ታዋቂው የእስፖርት ሰው ይድነቃቸው ተሰማ ሱዳን ከእግር ኳሱ አምባ ጠፍታ ከርማ ወደሜዳ ስትመለስ ያሳየችውን ድንቅ እርምጃ በተመለከተ የሰጡት አስተያየት፤ ማስገንዘቢያ፣ ማስጠንቀቂያና የእግር ኳሱን ሂደት ማሳያ ነው፡፡ ለኢትዮጵያ ደግሞ ዋና ማሳሰቢያ ነው!
“ቆመን ጠበቅናቸው ጥለውን አለፉ!” ነበር ያሉት፡፡ ነብሳቸውን ይማርና ዛሬ፤ ቆመን አልጠበቅናቸውም!
እየሄድን ነው!” እንላቸው ነበር፡፡ እንዴት ደስ ባላቸው!
እንደ አዲስ ዓመት ምላሽ “ከብረው ይቆዩን ከብረው” የምንባባልበት እንዲሆን እንመኛለን”
መልካም አዲስ ዓመት!!

Published in ርዕሰ አንቀፅ

የአዲሱ ጠ/ሚኒስትር አዲሱ አስተዳደር
የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በ2004 ዓ.ም መገባደጃ ላይ ህይወታቸው ማለፉን ተከትሎ የአገሪቱ ቀጣይ እጣ ፈንታ ብዙዎችን ማሳሰቡ አልቀረም፡፡ የዳያስፖራ ፖለቲከኞችና አንዳንድ ዓለም አቀፍ ተቋማት በኢህአዴግ ውስጥ የስልጣን ሽኩቻ እንደሚፈጠር ስጋታቸውን ገልፀው ነበር፡፡ በአገር ውስጥም ተመሳሳይ ስጋት የነበሯቸው ወገኖች አልነበሩም ማለት አይቻልም፡፡ ይሄ ስጋት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርና ምክትል ጠ/ሚኒስትር የነበሩት አቶ ኃይለማርያም ደሣለኝ በመስከረም 2005 ዓ.ም በጠ/ሚኒስትርነት ከተሾሙም በኋላ ለተወሰነ ጊዜ የቀጠለ ይመስላል፡፡ አንዳንድ የተቃዋሚ መሪዎችና የፖለቲካ ተንታኞች አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የሥልጣን ክፍተቱን ለመሙላት ለጊዜው ተቀመጡ እንጂ የጠ/ሚኒስትርነቱ ቦታ ከህወሐት እጅ እንደማይወጣ ተንብየው ነበር፡፡ ቢያንስ እስካሁን ግን ትንበያቸው የሰራ አይመስልም፡፡ በአዲሱ ህግ መሰረት ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ለአስር ዓመት (ሁለት ተርም) በሥልጣናቸው ላይ እንደሚቆዩ ይጠበቃል።
አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በኢህአዴግ ማዕከላዊ ኮሚቴ ምርጫ ተፎካካሪያቸውን (ብአዴን ያቀረባቸውን) አቶ ደመቀ መኮንንን በማሸነፍ ነው የጠ/ሚኒስትርነት ሥልጣኑን የያዙት፡፡ በድምፅ ብልጫ የተሸነፉት አቶ ደመቀ መኮንንም ከትምህርት ሚኒስትርነታቸው በተጨማሪ የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ቦታ ለማግኘት ችለዋል፡፡ ብዙም ሳይቆይ ግን የምክትል ጠ/ሚኒስትርነት ሃላፊነታቸውን በቅጡ እንዲወጡ በሚል ከትምህርት ሚኒስትርነታቸው ተነስተዋል፡፡ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም በአንድ ዓመት የሥልጣን ዘመናቸው በርካታ ሹም ሽሮችን አድርገዋል፡፡ ከሁሉም የሚቀድመው ግን በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የሚጠሩ ሁለት ተጨማሪ ባለስልጣናትን መሾማቸው ነው፡፡ ከኦህዴድ አቶ ሙክታር ከድር፣ ከህወኃት ደግሞ ዶ/ር ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል በሚኒስትርነት ከሚመሯቸው መስሪያ ቤቶች በተጨማሪ የምክትል ጠ/ሚኒስትርነት ሹመት አግኝተዋል፡፡ ይሄ ያልተለመደ አሿሿም ህገመንግስቱን የጣሰ ነው በሚል ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተቃወሙት ሲሆን ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም በበኩላቸው፤ የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር በህይወት ሳሉ የታሰበበት ጉዳይ እንደነበርና ሥራን በጥራትና በብቃት ለማከናወን ታልሞ የተደረገ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

የአቶ ኃይለማርያም አስተዳደር ትልቁ “ራስ ምታት”
ለአዲሱ የአቶ ኃይለማርያም መንግስት ከምንም በላይ ትልቅ ራስ ምታት የሆነበት “የሃይማኖት አክራሪነት” ጉዳይ ነው፡፡ ከእስልምና ምክር ቤት ምርጫ እና ከአወሊያ ት/ቤት ጋር ተያይዞ የተነሳው ውዝግብ “የሙስሊሙ መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ” አባላት መታሰርን ተከትሎ እየተባባሰ የመጣ ሲሆን “ድምፃችን ይሰማ” እና “የታሰሩት ይፈቱ” የሚሉ ተቃውሞዎች በየጊዜው ሲሰሙ ቆይተዋል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተቃዋሚ ፓርቲዎች አንዱ አጀንዳቸው መሆኑ ደግሞ መንግስትን ክፉኛ አስቆጥቶታል፡፡ በአመቱ መገባደጃ ግድም በደሴ ከተማ ግድያ የተፈፀመባቸው የሼክ ኑሩ ይማም ጉዳይም ነገሩን የበለጠ አባብሶታል፡፡ መንግስት ሼኩን አክራሪዎች ስለመግደላቸው በቂ ማስረጃ አለኝ ሲል፤ አንዳንድ ወገኖች ደግሞ ጉዳዩን “የመንግስት ድራማ ነው” ማለታቸው ይታወሳል፡፡ የአክራሪነት አጀንዳ በዚህ መልኩ አሁንም ድረስ አነጋጋሪነቱ ቀጥሏል፡፡ በ2006 መቋጫ ይበጅለት ይሆን?
ከ8 ዓመት በኋላ የተነሳው የሰላማዊ ሰልፍ እገዳ
ከ97 ምርጫ በኋላ ላለፉት 8 አመታት ታግዶ የቆየው ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ መብት የተፈቀደው ባሳለፍነው አመት ነበር፡፡ በግንቦት ወር በሠማያዊ ፓርቲ የተጀመረው የተቃውሞ ሠልፍ፤ በአንድነት ፓርቲ ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ ሠማያዊ ፓርቲም የጠየቃቸው አራት ጉዳዮች ምላሽ ባለማግኘታቸው በድጋሚ ሠላማዊ ሠልፍ መጥራቱ ይታወሳል፡፡ አንድነት ፓርቲ የ3 ወር የህዝባዊ ንቅናቄ መርሃ ግብር ዘርግቶ በ16 ያህል ከተሞች ሠላማዊ ሠልፎችና ህዝባዊ ስብሠባዎችን አድርጓል፡፡ “የሚሊየኖችን ድምፅ” በሚል ስያሜም አወዛጋቢ የሆነውን የፀረ ሽብር ህግ ለማሠረዝ እንቅስቃሴ ጀምሯል፡፡ ይሄንን ተከትሎም አዋጁ ከወጣ ከአራት አመት ገደማ በኋላ በኢቴቪ አዘጋጅነት ኢህአዴግና ተቃዋሚዎች በፀረ ሽብር ህጉ ላይ ትኩረትን የሳበ ጠንካራ ክርክር አድርገዋል - በዓመቱ መገባደጃ ላይ፡፡

“ፓርላማው ጥርስ አወጣ?” ወይስ ድሮም ነበረው?
ሌላው ዘንድሮ የታየ ጉልህ ለውጥ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ከፍተኛ መነቃቃት ማሳየቱ ነው፡፡ ባለፉት 21 አመታት ባልታየ መልኩ ፓርላማው የመንግስት አስፈፃሚ አካላትን የስራ ውጤት አጥብቆ ሲሞግትና ሲገመግም ተስተውሏል፡፡ ይሄን ያስተዋሉ አንዳንድ ፖለቲከኞች “ፓርላማው ዘንድሮ ጥርስ አወጣ” ሲሉ አፈጉባኤውን ጨምሮ አብዛኞቹ የምክር ቤቱ አባላት በዚህ አይስማሙም፡፡ “ፓርላማው ድሮም ጥርስ ነበረው” የሚሉት አባላቱ እስካሁን ያልታየው ሚዲያው ትኩረት ሰጥቶ ስለማይዘግብ ነው በማለት ይከራከራሉ፡፡ ከህወሐት የመጀመርያ መስራቾች አንዱ የሆኑት አቶ ስብሐት ነጋ ለአዲስ አድማስ በሰጡት አስተያየት፤ የምክር ቤቱን መነቃቃት ማጤናቸውን ጠቁመው “የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሥራውን በመጀመሩ የኢትዮጵያ ህዝብ እንኳን ደስ ያለው” ማለታቸው ይታወሳል፡፡ አሁን ብዙዎችን የሚያሳስባቸው ጥርስ አወጣ አላወጣም የሚለው ክርክር ሳይሆን የተጀመረው መነቃቃት ተጠናክሮ ይቀጥላል ወይስ እንደ ወረት ታይቶ ይጠፋል የሚለው ጉዳይ ነው፡፡ ለጊዜው ይሄን የሚያውቀው ደግሞ መንግስት ብቻ ነው ይላሉ - አስተያየት ሰጪዎች፡፡

“መንግስት ይከሰሳል” የተባለበት ዓመት
በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል የአማራ ተወላጆች መፈናቀልም በዓመቱ አነጋጋሪ ከነበሩ ክስተቶች ተጠቃሽ ነው፡፡ በወቅቱ የተፈናቀሉት ቁጥራቸው ከ3ሺህ የሚልቅ ሠዎች፤ በአማራ ክልል ፍኖተ ሠላም ከተማ በጊዜያዊነት እንዲጠለሉ ከተደረገ በኋላ፣ የክልሉ መንግስት አመራሮች “እኛ ሣናውቅ ነው የተፈናቀሉት” በማለት ወደነበሩበት እንዲመለሡ ተደርጓል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝም በይፋ ድርጊቱን በማውገዝ በድርጊቱ የተሣተፉ ወንጀለኞች ለፍርድ እንደሚቀርቡ በፓርላማ ገልፀዋል፡፡
ከዚሁ ጋር በተያያዘ መኢአድና ሠማያዊ ፓርቲ መንግስትን ለመክሠስ የሚያስችለንን ዝግጅት እያደረግን ነው ሲሉ በይፋ ያስታወቁ ሲሆን መንግስት በበኩሉ ተቃዋሚዎች ጉዳዩን ለፖለቲካዊ ጥቅማቸው እያዋሉት ነው ሲል ተችቷል፡፡ መንግስት ጥፋት ሲፈፅም ይከሰሳል ወይ የሚለውን በተመለከተ ግን ቁርጥ ያለ መልስ የምናገኘው ምናልባት ወደፊት ሊሆን ይችላል፡፡
ሶስቱ አነጋጋሪ የዓመቱ ምርጫዎች
በ2005 ዓ.ም ከተከናወኑ አበይት ፖለቲካዊ ጉዳዮች መካከል የአዲስ አበባ እና የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደሮች ምክር ቤት ምርጫ ይጠቀሳል፡፡ በሚያዚያ ወር በተካሄደው ምርጫ ዋናዎቹ ተቃዋሚዎች “ምርጫ ቦርድ ለጥያቄያችን ምላሽ አልሰጠንም” በሚል ራሣቸውን ያገለሉ ሲሆን በዚህም አጋጣሚ “33 ፓርቲዎች” በሚል የጋራ መሠባሠቢያ መድረክ ለመፍጠር ችለዋል፡፡ ኢህአዴግ በምርጫው በተወዳደረባቸው አካባቢዎች ሁሉ ማሸነፉን ምርጫ ቦርድ የገለፀ ቢሆንም ተቃዋሚዎች በበኩላቸው ኢህአዴግ ለብቻው ተወዳድሮ ለብቻው አሸንፏል በማለት ምርጫው “ፍትሃዊ” አልነበረም ሲሉ ተቃውመዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ ለአምስት አመት ያስተዳደሯትን ከንቲባ ኩማ ደመቅሳን አሰናብታ አዲሱን አቶ ድሪባ ከማልን የተቀበለችውም ባሳለፍነው ዓመት ነበር፡፡
የተጠናቀቀው አመት ከፖለቲካዊ ምርጫ ባሻገርም የሃገሪቱ ዋና ዋና ሃይማኖቶች መሪዎች ምርጫም አስተናግዷል፡፡ በጥቅምት ወር ላይ በውዝግብ የታጀበው የኢትዮጵያ እስልምና ምክር ቤት አመራሮች ምርጫ የተካሄደ ሲሆን በየካቲት ወር ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ ምርጫ ተካሂዷል፡፡ በእስልምና ምክር ቤት ምርጫ ሼህ ኪያር መሃመድ አማን በፕሬዚዳንትነት ሲመረጡ በፓትርያርክ ምርጫው አቡነ ማትያስ ተመርጠዋል፡፡

መንግስት ሙስና ላይ ያመረረበት ዓመት
ኢህአዴግ በሥልጣን ላይ በቆየባቸው 21 ዓመታት እንደ ዘንድሮ በሙስና ላይ አምርሮ አያውቅም ይላሉ አስተያየት ሰጪዎች፡፡ ነገሩ እውነት ይመስላል፡፡ በግንቦት ወር መጀመርያ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ከፍተኛ ሃላፊዎች፣ ሠራተኞች፣ ደላላዎችና ባለሃብቶች በከባድ የሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ታስረዋል፡፡ በሚኒስትር ማዕረግ የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር የነበሩት አቶ መላኩ ፋንታ፣ የህግ ክፍል ዳይሬክተር የነበሩት አቶ ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስ እንዲሁም የአቃቤ ህግ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር የነበሩት አቶ እሸቱ ወልደሠማያትን ጨምሮ ሌሎች የቅርንጫፍ ፅ/ቤት ሃላፊዎችና ሠራተኞች እንዲሁም ትላልቅ ባለሃብቶች በአጠቃላይ ከ60 በላይ ተጠርጣሪዎች ታስረው ጉዳያቸውን በፍ/ቤት እየተከታተሉ ይገኛሉ፡፡ ከታዋቂ ባለሃብቶች መካከልም የኬኬ ኃ.የተ.የግ.ማህ. ባለቤት አቶ ከተማ ከበደ፣ የኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል ባለቤት አቶ ስማቸው ከበደ፣ የነፃ ትሬዲንግ ባለቤት አቶ ነጋ ገ/እግዚአብሔር እና ሌሎችም ከተጠርጣሪዎቹ ውስጥ ይገኙበታል፡፡
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ኮርፖሬሽን ዘጠኝ የስራ አመራሮችም በሙስና ተጠርጥረው ክስ የተመሰረተባቸው በዚሁ ዓመት ነው፡፡ ከሙስና ጋር በተያያዘ የተለያዩ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናትም ከሃላፊነታቸው የተነሱ ሲሆን ከእነዚህም መካከል የፍትህ ሚኒስትሩ አቶ ብርሃነ ሃይሉ እንዲሁም የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ ዳሬክተርና ሁለት ምክትሎቻቸው ይገኙባቸዋል፡፡

መንግስት ከአቅሙ በላይ አቅዶ ይሆን? (የቤቶች ፕሮግራም)
ባለፈው ዓመት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በከፍተኛ ትኩረት ሠጥቶ ከተንቀሳቀሰባቸው ጉዳዮች መካከል በቀዳሚነት የሚጠቀሰው አዲሱ የቤት ፕሮግራም ነው፡፡ አንድ ሚሊዮን ሠዎች ይመዘገባሉ በተባለለት የቤት ፕሮግራም፣ 10/90፣ 20/80፣ 40/60 እና የማህበራት በሚል አራት ቦታ ተከፋፍሎ የቀረበ ነው፡፡ የቤት ፕሮግራሙ ውጤታማ ይሆናል አይሆንም የሚለው ጉዳይ ሲያወዛግብ የከረመ ሲሆን መንግስት በቁርጠኝነት አሣካዋለሁ ሲል ተቃዋሚዎች ደግሞ ስኬቱ ያጠራጥረናል ብለዋል፡፡ ከዚሁ የቤት ፕሮግራም ጋር በተያያዘ ተመዝጋቢዎች የቁጠባ ሂሳብ በመንግስት ባንክ ብቻ እንዲከፈቱ መደረጉ ለግል ባንኮች ስጋት እንደሆነ መነገሩ የሚታወስ ሲሆን የግል ባንኮች ብዙ ደንበኞቻቸውን እንዳጡም መግለፃቸው አይዘነጋም፡፡
2005 ዓ.ም እነዚህን ዋና ዋና አነጋጋሪና አወዛጋቢ ጉዳዮችን አስተናግዶ አልፏል፡፡ አዲሱ ዓመትስ? አብረን የምናየው ይሆናል፡፡

Page 11 of 16