አዲስ አበባ አራት ኪሎ ከፓርላማ ጀርባ የሚገኘው የመቃብር ስፍራ አጥር በመፍረሱና ዛፎች በመውደቃችው፣ መቃብሮች እየተናዱ የሙታን አፅሞች ከሳጥን ወጥተው ሜዳ ላይ እንደወዳደቁ ሁለት ሳምንት አለፋቸው፡፡ አዲስ አበባ መስተዳድር እና የመቃብር ስፍራውን የሚያስተዳድረው ደብር በጉዳዩ ላይ እየተወዛገቡ ነው፡፡ በፓርላማ ጀርባ ባለወልድ ቤ/ክርስትያን ቅጥር ግቢ አጠገብ በሚገኘው መንገድ ጠዋትና ማታ የሚመላለሱት ወ/ሮ አምሳለ ከበደ፤ የግቢው አጥር ለመንገድ ስራ ከፈረሰ ከአምስት አመት በላይ እንደሆነው ገልፀው፣ ሁለት ዛፎቹ ስራቸው እየተንሸራተተ ሲወድቁ መቃብሮች እየተፈነቃቀሉ መንገድ ላይ ወድቀዋል ብለዋል፡፡ መንገዶች ላይ የወዳደቀ የሙታን አጽም እያየን ነው የምናልፈው ያሉት ወ/ሮ አምሳለ፤ ሦስት ሳምንት ሆኖታል፤ የጭንቅላት፣ የእግር፣ የእጅ አጽም ያለ ክብር ወዳድቆ ማየት ልብን ይነካል ብለዋል፡፡

ከፍ ብለው የሚገኙት መቃብሮችም ተፈነቃቅለው ለመውደቅ አፋፍ ላይ ደርሰዋል በማለት የተናገረችው ወ/ሪት ቤተልሄም፤ ህፃናት የሙታንን አጽምና ጭንቅላት በእግራቸው እየመቱ ሲራመዱ ያሳዝናል ብላለች፡፡ ቤተሰብ ለማስታወሻ ብሎ ያስገነባቸው ሀውልቶች እግረኛ መንገድ ላይ ወድቀው በማየታችን ለደብሩ ሃላፊዎች ብንናገርም ምንም መልስ አልሰጡንም ብላለች ወ/ሪት ቤተልሄም፡፡ ልጃቸውን ከትምህርት ቤት ሲመልሱ ያገኘናቸው አቶ ሚኪያስ ዳንኤል በዚሁ መንገድ አዘውትረው እንደሚጠቀሙ ገልፀው፤ ከፍ ብሎ ከሚገኘው የመቃብር ስፍራ አጽሞች ወደ መንገድ መውደቅ የጀመሩት ከሁለት ሳምንት በፊት ነው ብለዋል፡፡

የሰው ልጅ አጽም ክብር አጥቶ ሜዳ ላይ ወድቆ ሰናይ፣ በሞት የተለዩ ቤተሰቦቻችንን እያሰብን እንሸማቀቃለን ያሉት አቶ ሚኪያስ፤ የደብሩ አስተዳደር ለሙታኑ ቤተሰቦች በማሳወቅ የሙታኑን አጽም እንዲያነሱ ማድረግ ነበረበት፤ ካልሆነም አጽሞቹን ሰብስቦ በክብር አንድ ቦታ መቅበር አለበት ብለዋል፡፡ የደብሩ ፀሐፊ የዚህ ችግር ሪፖርት አልደረሰኝም ያሉ ሲሆን፤ የደብሩ ተቆጣጣሪ አባ አክሊሉ ገ/አምላክ በበኩላቸው፤ የአዲስ አበባ መስተዳድር ለመንገድ ስራ ግንቡን እንዳፈረሰ ጠቅሰው፣ በዝናብ አፈሩ እየተናደ አጽሞቹ እንደወደቁ ተናግረዋል፡፡ ግንቡን መልሶ የመገንባት አቅም የለንም ያሉት አባ አክሊሉ፤ የአዲስ አበባ መስተዳድር ያፈረሰውን ግንብ የመገንባት ግዴታ አለበት፤ እኛ የወደቁትን አጽሞች ለቅመን በአንድነት እንቀብራለን ብለዋል፡፡ የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ሲሳይ ወርቅነህ፤ መንገዱ ሲገነባ ለደብሩ ካሳ እንደተከፈለ ጠቅሰው፤ በአስፋልቱ በኩል ያለውን አጥር መገንባት ያልጀመርነው ስምንት ያልተነሱ መቃብሮች ስላሉ ነው ብለዋል፡፡ በመንገድ ስራ ምክንያት ሳይሆን በዛፎች መውደቅ ሳቢያ የተፈነቃቀሉ መቃብሮችና የፈረሱ ግንቦች የደብሩን አስተዳደር እንጂ እኛን የሚመለከቱ አይደሉም ያሉት አቶ ሲሳይ፤ ወደ ግንፍሌ በሚያወጣው መንገድ ላይ ሁለት ትልልቅ ዛፎች ቢወድቁም የደብሩ አስተዳደር እስካሁን አላነሳቸውም ብለዋል፡፡

Published in ዜና

ነገ በእንግሊዝ ኒውካስትል በ2013 ‹ቡፓ ግሬት ኖርዝ ራን› ላይ የዓለማችን ምርጥ የረጅም ርቀት ሯጮች በግማሽ ማራቶን ከባድ ትንቅንቅ ሊያደርጉ ነው፡፡ በሁለቱም ፆታዎች በዋናነት የኢትዮጵያ ምርጥ የረጅም ርቀት ሯጮች ተፎካካሪነት ሲጠበቅ በርቀቱ አዳዲስ የዓለም ሪከርዶች የሚመዘገቡበት እድል የሰፋ መሆኑ እየተገለፀ ነው፡፡ በወንዶች የግማሽ ማራቶን ውድድሩ ላይ ኃይሌ ገብረስላሴ፤ ቀነኒሣ በቀለ እና የእንግሊዙ ሞፋራህ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ በግማሽ ማራቶን ውድድር በመገናኘት አስደናቂ ፉክክር ያደርጋሉ፡፡ በግማሽ ማራቶን ውድድሩ ኃይሌ ገብረስላሴ ካለው ልምድ አንፃር ከፍተኛ የማሸነፍ ግምት እንዳለው ቢገለፅም፤ በዓለም ሻምፒዮና በ5ሺ ሜትር እና በ10ሺ ሜትር ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎችን የወሰደው የእንግሊዙ ሞ ፋራህ ዓመቱን በስኬት ለመደምደም ማቀዱ እና በግማሽ ማራቶን ለመጀመርያ ጊዜ የሚሳተፍው ቀነኒሣ በቀለ በውጤታማነት ወደ ጎዳና ሩጫዎች ለመሸጋገር ተስፋ ማድረጉ ፉክክሩን ያጠናክረዋል፡፡ በሴቶች ምድብ በተለይ በ5ሺ ሜትር ውድድሮች ባላቸው ተቀናቃኝነት ዓለም የሚጓጓላቸው ጥሩነሽ ዲባባ እና መሰረት ደፋር በግማሽ ማራቶን ውድድር ለመጀመርያ ጊዜ መገናኘታቸውም ትኩረት ስቧል፡፡ በግማሽ ማራቶን ውድድር ጥሩነሽም ሆነ መሰረት ያን ያህል የዳበረ ልምድ እንደሌላቸው የገለፀው የአትሌቲክስ ዊክሊ ዘገባ፤ እርስ በራስ ለመሸናነፍ የሚያደርጉት ትንቅንቅ ግን ምናልባትም ክብረወሰን እንዲሰበር ምክንያት ሊሆን ይችላል ብሏል፡፡
ግማሽ ማራቶን በአጠቃላይ 21.0 975 ኪ.ሜ የሚሸፍን ውድድር ነው፡፡ በወንዶች ግማሽ ማራቶን የዓለም ሪኮርድን የያዘው ኤርትራዊው ዘረሰናይ ታደሰ በ2010 እ.ኤ.አ በፖርቱጋል ሊዝበን ባስመዘገበው 58 ደቂቃ ከ23 ሰኮንዶች ሲሆን ፤ በሴቶች ደግሞ የኬንያም ማሪ ኪታኒ በ2011 እ.ኤ.አ በዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ 1 ሰዓት ከ05 ደቂቃ ከ50 ሰኮንዶች ርቀቱን በማጠናቀቅ ሪከርዱን አስመዝግባለች፡፡ በኖቫ ኢንተርናሽናል የሚዘጋጀው ‹ቡፓ ግሬት ኖርዝ ራን› ከዓለማችን ግዙፍ የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድሮች በሁለተኛ ደረጃ የሚጠቀስ ሲሆን ነገ ከ56ሺ በላይ ስፖርተኞችን እንደሚያሳትፍ ሲታወቅ ራን› በ10ሺ ሜትር የኦሎምፒክ የነሐስ ሜዳልያ ተሸላሚ በሆነውና የቢቢሲ ኮሜንታተር በነበረው ብሬንዳን ፎስተር ከ32 ዓመታት በፊት የተመሰረተ ነው፡፡ የቡፓ ግሬት ኖርዝ ራን ውድድር ላይ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ከፍተኛ ስኬት ያላቸው ሲሆን በወንዶች ሶስት በሴቶች ደግሞ አራት አትሌቶች አሸናፊዎች ነበሩ፡፡ በወንዶች የግማሽ ማራቶን ውድድር በ2004 እኤአ ደጀኔ ብርሃኑ፤ በ2008 እኤአ ፀጋዬ ከበደ እንዲሁም በ2010 እኤአ ላይ ኃይሌ ገብረስላሴ ሲያሸንፉ፤ በሴቶች ምድብ ደግሞ በ2006 እና በ2010 እኤአ ላይ ብርሃኔ አደሬ ሁለቴ ማሸነፏ ሲታወስ፤ በ2005 እኤአ ላይ ደራርቱ ቱሉ፤ በ2008 እኤአ ላይ ጌጤ ዋሚ እንዲሁም ባለፈው አመት ጥሩነሽ ዲባባ አሸናፊዎች ነበሩ፡፡
ኃይሌ ከቀነኒሳ ከሞ ፋራህ
የ40 ዓመቱ አንጋፋ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ በነገው የግማሽ ማራቶን ውድድር ላይ በከፍተኛ የውድድር ደረጃ በተፎካካሪነት የመሰለፍ ብቃት እንዳለው ሲገልፅ ሁለቱን ተቀናቃኞቹን ቀላል አልፈትናቸውም ብሏል፡፡ በ2010 እኤአ ላይ በተመሳሳይ ስፍራ የግማሽ ማራቶን ውድድሩን በ59 ደቂቃ ከ33 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ በመጨረስ ያሸነፈው ኃይሌ ገብረስላሴ በግማሽ ማራቶን የዳበረ ልምድ ቢይዝም በሞ ፋራህ እና ቀነኒሳ ላይ ብልጫ ለማሳየት ከግዜ ወደ ጊዜ እየቀነሰ የመጣው አሯሯጡ እንቅፋት ሊሆንበት እንደሚችል ተገምቷል፡፡ ኃይሌ ገ/ስላሴ በ2006 እ.ኤ.አ በአሪዞና ግዛት አሜሪካ በ58 ደቂቃ ከ55 ሰኮንዶች ርቀቱን በመሸፈን ሪከርድ አስመዝግቦ ነበር፡፡ የ38 ዓመቱ ቀነኒሣ በቀለ ነገ በግማሽ ማራቶን የሚሮጠው በሩጫ ዘመኑ ለመጀመርያ ጊዜ ነው፡፡ በ‹ቡፓ ግሬት ኖርዝ ራን› ተሳትፎው ወደ ማራቶን ሯጭነት የሚሸጋገርበትን አዲስ ምእራፍ እንደሚከፈት የተናገረው ቀነኒሣ፤ ከ10 ዓመት በፊት የመጀመርያውን ዓለም አቀፍ ውድድር በኒውካስትል በተዘጋጀ አገር አቋራጭ ተሳትፎ ማሸነፉን አስታውሶ በነገው ግማሽ ማራቶን መሳተፉን እንደታላቅ ክብር እንደሚቆጥረው አስታውቋል፡፡ ኃይሌ እና ሞ ፋራህ በርቀት አይነቱ ከእሱ የተሻለ ልምድ እንደሚኖራቸው ያመነው ቀነኒሣ፤ከትራክ ውድድር ወደ ጎዳና ላይ ሩጫዎች የሚሸጋገርበትን ሁኔታ በሚያስመዘግበው ውጤት ለማነቃቃት እንደሚያስብም ተናግሯል፡፡ ቀነኒሣ በቀለ ከነገው የግማሽ ማራቶን ተሳትፎው በኋላ ወደ ማራቶን ፊቱን እንደሚያዞር ከመግለፁም በላይ በሚቀጥለው ዓመት በለንደን ማራቶን የመሳተፍ ፍላጎት እንዳለው እና ዋና እቅዱ እና ዓለማው በ2016 እኤአ ላይ በሚደረገው 31ኛው የብራዚል ኦሎምፒያድ በማራቶን መወዳደር መሆኑን አስታውቋል፡፡ እንግሊዛዊው ሞ ፋራህ በነገው የግማሽ ማራቶን ውድድር ለማሸነፍ እና ዓመቱን በስኬት የመዝጋት ፍላጎት እንዳለው ሲናገር ሰንብቷል፡፡ በሩጫ ዘመኑ ሶስተኛውን የግማሽ ማራቶን ውድድር የሚያደርገው ሞ ፋራህ ምናልባትም የኃይሌ እና የቀነኒሳ ተፎካካሪነት በመቋቋም ካሸነፈ በቡፓ ግሬት ኖርዝ ራን የውድድር ታሪክ ከ28 አመታት በኋላ ያሸነፈ እንግሊዛዊ ይሆናል፡፡ እንደ አትሌቲክስ ዊክሊ ሀተታ ሞ ፋራህ ለመጀመርያ ጊዜ የግማሽ ማራቶን ውድድር የሮጠው ከ2 ዓመት በፊት በኒውዮርክ ሲሆን በርቀቱ ፈጣን ሰዓቱን በዚሁ ውድድር በ60 ደቂቃ ከ23 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ ያስመዘገበ ነው፡፡
ኃይሌ፤ ቀነኒሣ እና ሞ ፋራህ ባለፉት 20 ዓመታት በረጅም ርቀት የአትሌቲክስ ውድድሮች ከፍተኛውን ውጤት ያስመዘገቡ የዓለማችን ምርጥ አትሌቶች ናቸው፡፡ በሞስኮው 14ኛው የዓለም ሻምፒዮና የእንግሊዙ አትሌት ሞ ፋራህ በ10ሺና በ5ሺ ሜትር ውድድሮች ደርቦ በማሸነፍ ከተሳካለት በኋላ አንዳንድ የመገናኛ ብዙሐናት የረጅም ርቀት ንጉስ መሆኑን የተናገሩት በሁለት ዓመት ልዩነት በአንድ ኦሎምፒክና ሁለት የዓለም ሻምፒዮናዎች ላይ የወርቅ ሜዳልያዎችን በመሰብሰቡ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የሁለቱንም ርቀቶች ክብረወሰን ባለመስበሩ አትሌት ሞ ፋራህ የእንግሊዝ አትሌቲክስ ንጉስ እንጅ የዓለም ሊሆን አለመቻሉ ግልፅ ይሆናል፡፡ ሞ ፋራህ ይህን አስመልክቶ በሰጠው አስተያየት ለረጅም ጊዜ አተኩሮ ሲሰራ የኖረው በዓለም ሻምፒዮና እና በኦሎምፒክ መድረኮች የወርቅ ሜዳልያዎችን ለማግኘት መሆኑን ገልፆ በቀነኒሣ በቀለ ለበርካታ ዓመታት ተይዘው የቆዩ የ10ሺ እና የ5ሺ ሜትር ሪከርዶችን የማሻሻል አቅም እንደሌለው በይፋ ተናግሯል፡፡ ከሦስቱ አትሌቶች የረጅም ርቀት ንጉስ የመባል ተፎካካሪነት ሊኖራቸው የሚችሉ ኢትዮጵያውያኖቹ ኃይሌ ገ/ስላሴ እና ቀነኒሳ በቀለ ናቸው፡፡
በዓለም አቀፍ ውድድሮች ባለው ልምድ 23 ዓመታትን ያስቆጠረው ኃይሌ ገብረስላሴ ቀዳሚው ሲሆን ቀነኒሳ የ21 ዓመት እንዲሁም ሞፋራህ ከ10 ዓመት ያነሰ ልምድ በመያዝ ይከተሉታል፡፡ በዓለም ሻምፒዮናዎች፤ በኦሎምፒክ እና በተለያዩ ዓለም አቀፍ ውድድሮች ከ25 በላይ የወርቅ ሜዳልያዎች በመሰብሰብ ቀነኒሣ ከፍተኛውን ስኬት ያስመዘገበ ሲሆን ኃይሌ ገብረስላሴ እስከ 15 የወርቅ ሜዳልያዎች በማስመዝገብ ሞ ፋራህ ደግሞ ከ7 የማይበልጡ የወርቅ ሜዳልያዎችን በመሰብሰብ በሰፊ ርቀት ይከተላሉ፡፡ ቀነኒሳ በቀለ በትራክ እና የአገር አቋራጭ ውድድሮች፤ ኃይሌ ገብረስላሴ በትራክ እና የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድሮች እንዲሁም ሞፋራህ በትራክ ውድድር ብቻ ባላቸው ውጤታማነት ይታወቃሉ፡፡ ኃይሌ ገብረስላሴ በሩጫ ዘመኑ ከ2 ማይል እስከ ማራቶን በ17 አይነት የውድድር መደቦች ከ27 በላይ ክብረወሰኖችን በማስመዝገብ ከፍተኛ ለውጥ በስፖርቱ ላይ መፍጠር ችሏል፡፡ ቀነኒሳ በቀለ በ5 የውድድር መደቦች ስድስት ክብረወሰኖችን ያስመዘገበ ሲሆን በ10ሺ እና በ5ሺ ሜትር የያዛቸው ሪከርዶች ለረጅም አመት ሳይሰበሩ በመቆየታቸው ተደንቆበታል፡፡ ሞ ፋራህ በአውሮፓ ደረጃ የተመዘገቡ ሪከርዶች እንጅ ዓለም አቀፍ ክብረወሰን የለውም፡፡
ጥሩነሽ ዲባባ ከመሰረት ደፋር
ጥሩነሽ ዲባባ እና መሰረት ደፋር በ5ሺ ሜትር ባላቸው ትንቅንቅ ከፍተኛ ትኩረት በመላው ዓለም ያገኛሉ፡፡ ነገ ግን ብዙ የዳበረ ልምድ በሌላቸው የግማሽ ማራቶን ውድድር የሚገናኙት ለመጀመርያ ጊዜ ነው፡፡ አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ ባለፈው ዓመት በቡፓ ግሬት ኖርዝ ራን በግማሽ ማራቶን ውድድር ላይ በሩጫ ዘመኗ ለመጀመርያ ጊዜ ስትሳተፍ ያሸነፈችው ርቀቱን በ1 ሰዓት ከ07 ደቂቃ ከ35 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ በማጠናቀቅ ነበር፡፡ አትሌት መሰረት ደፋር በበኩሏ ዘንድሮ በኒውኦርሊዬንስ በሮጠችው የግማሽ ማራቶን ያሸነፈቸው ከጥሩነሽ ሰዓት በ10 ሰከንዶች ፈጥና በመግባት ሲሆን ያስመዘገበችው 1 ሰዓት ኮ7 ደቂቃ ከ25 ሰኮንዶች የሆነ ጊዜ ነው፡፡
የጥሩነሽ እና የመሠረት አስደናቂ ፉክክር በሩጫ ዘመናቸው ባስገኙት ስኬት በማነፃፀር መታዘብ ይቻላል፡፡አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ በኦሎምፒክ መድረክ በ10ሺ እና በ5ሺ ሜትር ውድድሮች 3 ወርቅና 2 ነሐስ በመሰብሰብ ሲሳካለት መሰረት ደፋር በኦሎምፒክ 2 ወርቅና 1 የነሐስ ሜዳልያ ብቻ አላት፡፡ ለዓለም ሻምፒዮና ጥሩነሽ ዲባባ 5 የወርቅ ሜዳልያዋን ስትሰበስብ መሠረት ደፋር 2 ወርቅ፣ 2 ነሐስ አስመዝግባለች፡፡ መሠረት በዓለም የአትሌቲክስ ፍጻሜ ውድድር 9 ወርቅ እና 1 የብር ሜዳልያ በመሰብሰብ ሲሳካለት ጥሩነሽ ያላት1 የወርቅ 3 የብር 1 የነሐስ ነው ፡፡ በዓለም የቤት ውስጥ ውድድር መሠረት 4 ወርቅ 1 ብርና 1 ነሐስ ሜዳልያ ስትወስድ ጥሩነሽ በዚህ ውድድር ብዙም ውጤት የላትም፡፡ ጥሩነሽ በሩጫ ዘመኗ 7 የዳይመንድ ሊግና 7 የጐልደን ሊግ ሩጫዎችን ስታሸንፍ መሠረት ደፋር በበኩሏ 6 የዳይመንድ ሊግና 6 የጐልደን ሊግ ውድድሮችን አሸንፋለች፡፡ ጥሩነሽ በ5 ሺ ሜትር እና በ15 ካ.ሜ የጐዳና ላይ ሩጫ ሁለት የዓለም ክብረወሰኖች ሲኗሯት መሠረት በቤት ውስጥ ውድድር የ3ሺ እና የ5ሺ ሜትር ክብረወሰኖችን ይዛለች፡፡ አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ በዓለም አትሌቲክስ በ10ሺ ሜትር በ1360 ነጥብ ከዓለም አንደኛ፣ በጐዳና ላይ ሩጫ ለ1260 ነጥብ 1ኛ፣ በ5ሺ ሜትር በ1360 ነጥብ 2ኛ እንዲሁም በሁሉም የአትሌቲክስ ውድድር በ1392 ነጥብ ከዓለም 11ኛ ነች፡፡ አትሌት መሠረት ደፋር በ5ሺ ሜት በ1392 ነጥብ 1ኛ፣ በ10ሺ ሜትር በ1271 ነጥብ ዘጠነኛ እንዲሁም በሁሉም የአትሌቲክስ ውድድር በ13 ነጥብ ከዓለም 9ኛ ደረጃ ላይ ናት፡፡

ከአልጄርያ፤ከቱኒዚያ፤ ከጋና፤ ከናይጄርያ ወይስ ከአይቬሪኮስት
በ2014 እኤአ ላይ ብራዚል በምታስተናግደው 20ኛው የዓለም ዋንጫ ላይ አፍሪካን በመወከል የሚሳተፉ 5 ብሄራዊ ቡድኖች የሚለየው የጥሎ ማለፍ ምእራፍ የጨዋታ ድልድል የፊታችን ሰኞ የሚወጣ ሲሆን ኢትዮጵያ ከማን ጋር ልትገናኝ ትችላለች የሚለው ጉዳይ አነጋጋሪ ሆኗል፡፡ ኢትዮጵያ በሚቀጥሉት ሁለት ወራት በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ምስራቅ አፍሪካን በመወከል ለዓለም ዋንጫ የምታልፍበትን እድል በ180 ደቂቃዎች ትወስናለች፡፡
የጥሎ ማለፉ ድልድል አስቀድሞ ካይሮ ውስጥ በሚገኘው የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ዋና ፅህፈት ቤት እንደሚደረግ ቢገለፅም በከተማዋ ባለው አለመረጋጋት በደቡብ ግብፅ በምትገኘው ሉክሰር ከተማ ለማውጣት መታቀዱ ተገልጿል፡፡ ባለፈው ሐሙስ ለዚሁ የጥሎማለፍ የጨዋታ ድልድል የሚያስፈልገው ወርሃዊው የፊፋ የእግር ኳስ ደረጃ የታወቀ ሲሆን ለጥሎ ማለፍ ምዕራፉ የበቁት 10 ብሄራዊቡድኖች በእጣ አወጣጥ ስነስርዓቱ በሁለት ማሰሮዎች የሚመደቡበት ሁኔታ ከዚሁ ጋር ተያይዞ ይፋ ሆኗል፡፡ በአሳዛኝ ሁኔታ ከ10ሩ ብሄራዊ ቡድኖች አንዷ የነበረችው ኬፕቬርዴ በምድቧ ከቱኒዚያ ጋር ባደረገችው የመጨረሻ ጨዋታ ተገቢ ያልሆነ ተጨዋች በማሰለፏ ውጤቷ ሲሰረዝባት በምትኳ ቱኒዚያ ለጥሎ ማለፉ ከደረሱት 10 ብሄራዊ ቡድኖች አንዷ እንድትሆን መወሰኑንም ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር ፊፋ አስታውቋል፡፡ ከኬፕቨርዴ መባረር በኋላ በወርሃዊው የፊፋ የእግር ኳስ ደረጃ መሰረት በሁለቱ የእጣ ማውጫ ማሰሮዎች የሚመደቡት አምስት አምስት ብሄራዊ ቡድኖች በከፍተኛ ደረጃቸው በማሰሮ 1 አይቬሪኮስት ፤ ጋና፤ አልጄርያ፤ ቱኒዚያ እና ናይጄርያ ሲቀመጡ በዝቅተኛ ደረጃቸው በማሰሮ 2 ግብፅ፤ ቡርኪናፋሶ፤ ካሜሮን፤ ሴኔጋል እና ኢትዮጵያ ናቸው፡፡ከትናንት በስቲያ በወጣው የፊፋ ወርሃዊ የእግር ኳስ ደረጃ ኢትዮጵያ ባለፈው ወር ከነበረችበት ደረጃ ዘጠኝ እርከኖችን በማሻሻል በአፍሪካ 25ኛ በዓለም 93ኛ ደረጃ ላይ ነች፡፡ አይቬሪኮስት በአፍሪካ 1ኛ በዓለም 19ኛ፤ ጋና በአፍሪካ 2ኛ በዓለም 24ኛ፤አልጄርያ በአፍሪካ 3ኛ በዓለም 28ኛ፤ ናይጄርያ በአፍሪካ 4ኛ በዓለም 36ኛ፤ ቱኒዚያ በአፍሪካ 7ኛ በዓለም 46ኛ ፤ ግብፅ በአፍሪካ 8ኛ በዓለም 50ኛ ፤ ቡርኪናፋሶ በአፍሪካ 9ኛ በዓለም 51ኛ እንዲሁም ሴኔጋል በአፍሪካ 11ኛ በዓለም 66ኛ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ወደ የዓለም ዋንጫ ለማለፍ በአፍሪካ ዞን በ ብሄራዊ ቡድኖች መካከል የሚደረገው የደርሶ መልስ ትንቅንቅ ላይ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከአራት የአፍሪካ ግዙፍ ብሄራዊ ቡድኖች ጋር መገናኘቱ በከፍተኛ ደረጃ በማነጋገር ላይ ይገኛል፡፡ በርካታ የስፖርት ቤተሰብ በጥሎ ማለፍ የደርሶ መልስ ትንቅንቁ ኢትዮጵያ ከየትኛውም ቡድን ጋር ተደልድላ የመጀመርያውን ጨዋታ ከሜዳ ውጭ የመልሱን ጨዋታ ደግሞ በሜዳዋ ላይ እንድታደርግ እየተመኙ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድኑ ለጥሎ ማለፉ ሁለት ጨዋታዎች በከፍተኛ ትኩረት እና በሙሉ አቅም እንዲዘጋጅ እና ቢያንስ ሁለት የወዳጅነት ጨዋታዎችን ለአቋም መፈተሻ ማድረግ እንደሚኖርበትም ይመክራሉ፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ሰኞ በሚወጣው የጥሎ ማለፍ የጨዋታ ድልድል በማሰሮ 1 ከሚገኙት አምስት ግዙፍ የአፍሪካ ብሄራዊ ቡድኖች ጋር የሚፋጠጥበት እድል ሲኖረው ተጋጣሚዎቹ አይቬሪኮስት ፤ ጋና፤ አልጄርያ፤ ቱኒዚያ እና ናይጄርያ ናቸው፡፡ አንዳንድ አስተያየት ሰጭዎች የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በጥሎ ማለፍ ድልድሉ ከግብፅ ጋር ላይገናኝ መቻሉ ያስደሰታቸው ቢሆንም ከሁለቱ የሰሜን አፍሪካ ብሄራዊ ቡድኖች አልጄርያ እና ቱኒዚያ ጋር የምትገናኝበት እድል መኖሩ አስግቷቸዋል። ከሰሜን አፍሪካ ብሄራዊ ቡድኖች ባሻገር የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በርካታ የፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ስብስብ ከሚይዙት የምእራብ አፍሪካ ተወካዮች ጋና እና አይቬሪኮስት ጋር መገናኘቷን በስጋት የሚመለከቱ ስፖርት አፍቃሪዎች ደግሞ ከምእራብ አፍሪካ ቡድኖች በተለይ ከናይጄርያ ጋር ብትገናኝ ምርጫቸው እንደሆነ ይገልፃሉ፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ለመጨረሻው የጥሎ ማለፍ ምእራፍ መብቃቱ በራሱ ታላቅ ታሪክ እንደሆነ የሚያሰምሩበት አስተያየት ሰጭዎች በበኩላቸው ዋልያዎቹ በዓለም ዋንጫ ከሚሳተፉት የዓለም ምርጥ 32 ብሄራዊ ቡድኖች መሆኑ ካልቀረ ከአፍሪካ 10 ምርጥ ቡድኖች አንዱን አሸንፎ ማለፉ ተገቢ ፈተና ነው በማለት ሰኞ የሚወጣውን ድልድል በጉጉጉት ይጠባበቃሉ፡፡
ኢትዮጵያ በጥሎ ማለፍ የጨዋታ ድልድሉ ልትገናኛቸው ከምትችላቸው አምስት የአፍሪካ ብሄራዊ ቡድኖች ጋር ያላት የውጤት ታሪክ ተቀማጭነታቸውን በዩናይትድ ኪንግደም ባደረጉ የእግር ኳስ ታሪክ እና ስታስቲካዊ መረጃዎች አሰባሳቢ ባለሙያዎች ተቋም በሆነው ኤኤፍኤስ ተሰርቶ 11v11.com በተባለ ድረገፅ የተቀመጠው መረጃ ከዚህ በታች የቀረበውን ይመስላል፡፡
ኢትዮጵያ ከአልጄርያ - በ4 የአፍሪካ ዋንጫ ጨዋታዎች ተገናኝተው እኩል አንድ ጊዜ ሲሸናነፉ ሁለት ጊዜ አቻ ተለያይተዋል፡፡ ጨዋታዎቹ በ1968 እኤአ ላይ ኢትዮጵያ 3ለ1 ያሸነፈችበት፤ በ1982 እና በ1994 እኤአ ለሁለት ጊዚያት ያለምንም ግብ አቻ የተለያዩበት እና በ1995 እኤአ ላይ አልጄርያ 2ለ0 ያሸነፈችበት ናቸው፡፡
ኢትዮጵያ ከጋና - በአንድ የአፍሪካ ዋንጫ እና በሌላ ኢንተርናሽናል ግጥሚያ ለሁለት ጊዚያት ተገናኝተው እኩል አንድ ጊዜ ተሸናንፈዋል፡፡ በ1963 እኤአ በአፍሪካ ዋንጫ ጨዋታ ጋና 2ለ0 ስትረታ በ1996 ደግሞ በኢንተርናሽናል ግጥሚያ ኢትዮጵያ 2ለ0 አሸንፋለች፡፡
ኢትዮጵያ ከናይጄርያ - በታሪካቸው 6 ጊዜ ተገናኝተው ናይጄርያ አራቱን ስታሸንፍ ኢትዮጵያ አንድ ጊዜ አሸንፋ በአንድ ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል፡፡ ናይጄርያ ድል ያደረገችባቸው ጨዋታዎች በ2013 እኤአ በአፍሪካ ዋንጫ ላይ 2ለ0፤ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያዎች በ2011 እኤአ 4ለ0 ፤ በ1993 እኤአ 6ለ0 እንዲሁም በ1982 በአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ጨዋታ 3ለ0 የተመዘገቡት ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ ያሸነፈችበት ብቸኛ ጨዋታ በ1993 እኤአ ላይ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ 1ለ0 ያስመዘገበችው ሲሆን በ2011 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ደግሞ 2ለ2 አቻ ተለያይተዋል፡፡
ኢትዮጵያ ከአይቬሪኮስት - በታሪካቸው በ3 የአፍሪካ ዋንጫ ጨዋታዎች ተገናኝተው ሁለቱን አይቬሪኮስት ስታሸንፍ ኢትዮጵያ አንዱን ድል አድርጋለች፡፡ በ1968 እኤአ ላይ ኢትዮጵያ 1ለ0 ስታሸንፍ በተመሳሳይ ወቅት አይቬሪኮስት 1ለ0 ረትታለች፡፡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ በሰፊ የግብ ልዩነት ሽንፈት ተብሎ በሪከርድ የተመዘገበው ሌላው ግጥሚያ በ1970 እኤአ አይቬሪኮስት 6ለ1 ያሸነፈችበት ነው፡፡
ኢትዮጵያ ከቱኒዚያ - በአፍሪካ ዋንጫ እና በዓለም ዋንጫ ዋና ውድድር እና የማጣርያ ጨዋታዎች እንዲሁም በተለያዩ ኢንተርናሽናል የወዳጅነት ጨዋታዎች 9 ጊዜ ተገናኝተው ቱኒዚያ 4 ጊዜ እንዲሁም ኢትዮጵያ 3 ጊዜ ሲያሸንፉ በሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል፡፡ ኢትዮጵያ ያሸነፈችባቸው ሶስት ጨዋታዎች በአፍሪካ ዋንጫ በ1962 እኤአ ላይ 4ለ2፣ በ1963 እኤአ ላይ 4ለ2 እንዲሁም በወዳጅነት ጨዋታ በ1967 እኤአ ላይ 2ለ1 ያሸነፈችባቸው ነበሩ፡፡ ቱኒዚያ የረታችባቸው 4 ጨዋታዎች ደግሞ በ1964 እኤአ ላይ በወዳጅነት ጨዋታ 3ለ2፣ በአፍሪካ ዋንጫ ጨዋታ በ1965 እኤአ 4ለ0፣ በ1990 እኤአ 2ለ0 እንዲሁም በዓለም ዋንጫ የማጣርያ በ1993 እኤአ 3ለ0 በሆነ ውጤት የተመዘገቡ ናቸው፡፡ በአቻ ውጤት የተለያዩባቸው ሁለት ጨዋታዎች ደግሞ በዓለም ዋንጫ የማጣርያ ጨዋታ በ1992 እኤአ 0ለ0 የተለያዩበት እና በ2013 እኤአ ላይ በወዳጅነት ጨዋታ አንድ እኩል አቻ የወጡበት ናቸው፡፡

 

Monday, 16 September 2013 08:25

‘ቀይ ወጥ’ እና እንቁጣጣሼ

አዝናለሁ!
እንቁጣጣሽ ‘አመት ጠብቃ የምትመጣ ጭንቀት’ ናት - ለኔ ፡፡
‘እንቁጣጣሽ፣ እንኳን መጣሽ
በአበቦች መሃል፣ እንምነሽነሽ…’
የሚለውን ዘፈን ስሰማ፣ ደስታ ሳይሆን ጭንቀት ነው በደም ስሬ የሚዘዋወረው፡፡ መስከረም በጠባ ቁጥር፣ እንቁጣጣሽ ይዛብኝ የምትመጣውን ጭንቀት ማስተናገድ እጣዬ ከሆነ አመታት አልፈዋል። “እንኳን አደረሰህ!” ብሎ መልካም ምኞት እኔን አይመለከተኝም፡፡ አመታዊ ጭንቀት መጣች ብዪ ልደሰት አልችልም!! ምንም ማድረግ አልችልም፡፡
እርግጥ ድሮ ግን እንዲህ አልነበርኩም፡፡ የዛሬን አያድርገውና ድሮ ድሮ እንቁጣጣሽ በጉጉት የምጠብቃት የፍንደቃ አውዳመት ነበረች፡፡ አመት ጠብቃ ይዛው እስክትመጣ የምጓጓለት፣ የራሷ የሆነ ድምቀት ነበራት፡፡ የሆነ ጊዜ ላይ ግን፣ እንቁጣጣሽ ድምቀት ትታ ጭንቀት ይዛልኝ መምጣት ጀመረች፡፡
ጊዜው 1984 ነበር፡፡
የአስራ አንድ አመት ልጅ እያለሁ ከመጣችው እንቁጣጣሽ በኋላ እየመጡ የሄዱት (ይቺኛዋን ጨምሮ) ሃያ ሁለት እንቁጣጣሾች ሁሉ፣ ለእኔ ጭንቀቶች ናቸው፡፡
አስራ አንደኛዋ እንቁጣጣሽ…
እንቁጣጣሽ… የኔ እንቁ… የኔ ፍልቅልቅ… የኔ ብዙ ብር… የኔ ብዙ ሳንቲም… የኔ መትረፍረፍ… እንቁጣጣሼ መጣች!!
ሰኔ ግም ሲል ጀምሮ በጉጉት ስናፍቃት ፣ በተስፋ ስጠብቃት ፣ ስዘጋጅላት፣ ሳቅድላት፣ መቼ በመጣች ስላት የከረምኳት እንቁጣጣሽ ደረሰች፡፡ አልነጋ ብሎ ከሚጎተተው፣ ከዚህ ዘልዛላ ሌሊት በኋላ ወደ ቤቴ ሰተት ብላ ልትገባና ብር በብር… ሳንቲም በሳንቲም ልታደርገኝ ከደጃፍ ቆማለች!!
እኔም ሆንኩ ታናናሽ እህቶቼ፣ እንቁጣጣሽ የምታመጣልንን አመታዊ ጸጋ ለመቀበል ዝግጅታችንን አጠናቀናል፡፡ በቀይ በቢጫ የደመቁ ስዕሎቻችንን ይዘን መንጋቱን እንጠባበቃለን፡፡
“የምን ስዕል ላይ ማፍጠጥ ነው?!.. አትተኙም እንዴ?” አለች እናቴ ቆጣ ብላ፡፡
“እህ!... ገና እኮ ነው… ትንሽ እንጫወት እንጂ?... ደሞ ከለር ያልቀባኋት አበባ አለች… ቀብቼ ከጨረስኩ በኋላ…” በማለት የተቃውሞ ድምጼን ማሰማት ጀመርኩ፡፡
ምናለ የእናቴን ትዕዛዝ በተቀበልኩ ኖሮ?!... ምናለ ድምጼን አጥፍቼ አልጋ ውስጥ በገባሁ ኖሮ?!... ምናለ ያንን ቀለብላባ ምላሴን የሆነ ነገር በቆረጠው ኖሮ?!
አባባ ከመኝታ ቤት ሆኖ የምለውን ሰምቶ ኖሮ፣ እንደተኮሳተረ በፒጃማ ከተፍ አለ፡፡
“ተናግሪያለሁ!... በኋላ ጉድ እንዳይፈላ!!... እንደማንም መረን አደግ፣ በየሰው ደጃፍ እየተለገባችሁ እንዳታዋርዱኝ!!... ከእኔ፣ ከናታችሁና ካጎታችሁ በቀር እንቁጣጣሽ ብላችሁ ከሌላ ሰው ፊት ብትቆሙ ጉድ ይፈላል!!...” አለ አባባ በሚያስፈራ አንደበት፡፡
“ኧረ ምን በወጣን!... እኛ ለማኝ ነን እንዴ?... ይሄው ሶስት ስዕል ብቻ ነው ያዘጋጀሁት” እህቴ አበባ የተሳለባቸውን ወረቀቶች ከፍ አድርጋ ይዛ ተናገረች። ደግነቱ አባቴ ለማጣራት አልሞከረም እንጂ፣ እኔ እንኳን ስድስት ስዕሎች ነበር ያዘጋጀሁት፡፡ የአባባን ትዕዛዝ ለማክበር ቃል ገብተን አልጋ ውስጥ ገባን፡፡
ሲነጋ…
እንቁጣጣሽን ገድ ያልኩት ከአባባ ባገኘሁት አንድ ብር ነው፡፡ እናቴም “እንቁጣጣሽ!” ብዬ የሰጠኋትን የአበባ ስዕል በአድናቆት እያየች፣ “በያመቱ ያምጣህ!” በማለት 50 ሳንቲም አሻረችኝ። ከአባባ በተሰጠን ፍቃድ መሰረት፣ ከእህቶቼ ጋር ወደ አጎታችን ቤት በማምራት አንድ አንድ ብር ተቀብለን እንደወጣን፣ እግረመንገዴን ከጋሽ ጣሴ ስሙኒ ሸቀልኩ፡፡ እማማ የሰራሽም ስልሳ ሳንቲም ለቀቁብኝ፡፡
እነ አባባ አክስቴ ቤት በግ ሊያሳርዱ እስከሚሄዱ ጠበቅኩና ከግቢያችን ሹልክ ብዬ ወጣሁ፡፡ በስማም!!... ጓደኞቼ ሁሉ ከወዲያ ወዲህ እየተራወጡ ነፍ ብር ይሸቅላሉ፡፡ እኔስ ምኔ ሞኝ ነው!?... ሮጥ ሮጥ ብዬ መስራቴን ቀጠልኩ፡፡ በስተመጨረሻ ግን ለእንቁጣጣሽ ያዘጋጀኋቸውን ስዕሎቼን ጨረስኩ፡፡ ተናደድኩ!! ምን አይነቱ ጌጃ ነኝ?... ለምንድን ነው አስር ስዕሎች ያላዘጋጀሁት?... ለሚቀጥለው ግን ሃያ ምናምን ነው የማዘጋጀው፡፡ እስከዛው ግን፣ በስዕል እጥረት ሽቀላ አያመልጠኝም፡፡ ለእናቴ የሰጠኋትን ስዕል ከሼልፉ ላይ ወስጄ ለቲቸር ጸደይ ሰጠኋትና ሽልንግ አሻረችኝ፡፡ ከዛም ከዳኒ ሁለት ስዕሎች በስሙኒ ሂሳብ ገዝቼ፣ በላይኛው ቅያስ በኩል ሄጄ እንቁጣጣሽ አልኩበት፡፡
ረፋድ ላይ…
ከመንደራችን መሃል ያለችው ጉብታ ላይ ቁጭ ብዬ፣ ያገኘሁትን ገንዘብ መቁጠር ጀመርኩ፡፡
በስማም!!... እንደዘንድሮ አይነት አሪፍ እንቁጣጣሽ አይቼ አላውቅም!!
ልጥጥ ነኝ!!
ለማስቲካና ከዳኒ ገዝቼ እንቁጣጣሽ ላልኩባቸው ተጨማሪ ሁለት ስዕሎች ያወጣሁት ወጪ ተቀናንሶ፣ ሰባት ብር ከስልሳ ሳንቲም አግኝቻለሁ!! ይህ ብር፣ በአስራ አንድ አመታት የህይወት ቆይታዬ በእጄ የያዝኩት ከፍተኛው ገንዘብ ነው፡፡ በዚያ ላይ ደግሞ የራሴ ነው፡፡ እንደፈለግኩ የማደርገው የግል ገንዘቤ ነው!!
በሰባት ብር ከስልሳ ሳንቲሜ ምን ማድረግ እንዳለብኝ ማሰብ ጀመርኩ፡፡ ቀጭ ቀጭ እስክርቢቶ ልግዛ?... ቀዩዋን መነጽር ልግዛ?... ለወላጆች ቀን መንበሽበሻ ላቆየው?... አስማተኛ ሲመጣ ልይበት?... ጸጉሬን ፓንክ ልቆረጥበት? (እናቴ ነበረች የምትላጨኝ)… እየቆጠብኩ የህንድ ፊልም ልይበት?... ወይስ ምን ላድርግበት?...
ጨነቀኝ!... በጣም በጣም ጨነቀኝ!... ገንዘቤን አስራ ምናምን ጊዜ ደጋግሜ እየቆጠርኩ፣ መቶ ምናምን እቅድ ማውጣትና ማግባት ቀጠልኩ። ገንዘብ ሳገኝ እንዲህ አደርጋለሁ ስላቸው የነበሩ እቅዶቼ ሁሉ ተምታቱብኝ፡፡ ምን አይነት እዳ ነው?!
ብሬ አለመጉደሉን ለሀያ ምናምነኛ ጊዜ በመቁጠር ላይ እያለሁ የሆነ ድምጽ ሰምቼ በድንጋጤ ክው አልኩ፡፡ እርግጠኛ ነኝ አስቻለው ነው፡፡ አስቻለው የሰፈራችን ጉልቤ ነው፡፡ አምና ለመስቀል በዓል ሆያ ሆዬ ብለን ያገኘነውን ብር ቀምቶናል፡፡ ይሄ ዱርየ!... አሁንም ሊቀማኝ መጣ!
ሰባት ብር ከስልሳዪን ጭምድድ አድርጌ ይዤ ቀና ስል፣ አስቻለውን ሳይሆን ዳዊትን ከአጠገቤ ቆሞ አየሁት፡፡ ተመስገን አምላኬ!! ዳዊት ጓደኛየ ነው፡፡
“ስንት ሸቀልሽ?” አለኝ እጅ እጄን እያየ፡፡
“አንቺስ?” መልሼ ጠየኩት፡፡
“አንድ አስራ ምናምን… አንቺስ?” አለ በፍጥነት።
ትንሽ ቀናሁ፡፡ ብዙ ስእሎች ባዘጋጅ ኖሮ፣ ከዳዊት በላይ ብር አገኝ ነበር፡፡
“አስራ ምናምን” አልኩት ከእሱ ላለማነስ፡፡
“አሪፍ ነዋ!... ይበቃናል!” አለ ዳዊት ፈገግ ብሎ፡፡
“ይ… ይበቃናል… ለምኑ ነው የሚበቃን?” ኮስተር አልኩበት፡፡
“ለቀይ ወጥ ነዋ!”
የኔ ነገር!... ረስቼው ነው እንጂ፣ እንቁጣጣሽ ብለን ስንጨርስ በሽር ሱቅ ጋ ልንገናኝ ተቀጣጥረን ነበር፡፡ ዳዊት ግን ጎበዝ ነው፡፡ ገና በአንደኛው ሴሚስተር የተባባልነውን አስታውሶ መምጣቱ ደነቀኝ፡፡ ያኔ የአክስቱ ባል ከሃረር መጥቶ እያለ፣ የሆነ ሆቴል ወስዶ የጋበዘው ቀይ ወጥ እንዴት እንደሚጥም ሲነግረኝ፣ እንዴት እንደጎመጀሁ አልረሳውም፡፡ እርግጥ ያልጎመጀሁ ለመምሰል ሞክሬ ነበር፡፡
“ዴቭ ደሞ ጉረኛ ነህ!... እኛ ቤት ቀይ ወጥ ተሰርቶ የማያውቅ መሰለህ!?” አልኩት፡፡
“የሆቴል ቀይወጥ፣ እንደ ቤት ቀይ ወጥ መሰለህ እንዴ?... ብታየውኮ… በስማም!... ደሞ የአጥንቱ ብዛት!.. ካላመንከኝ ስኔፉን አሽተው?” ብሎ ቀይ ወጥ የበላበትን እጁን ጣቶች አንድ በአንድ አሸተተኝ፡፡ አቤት ሽታው!! የሆነ ተንኮለኛ ነገር አይደለ!?... ሆን ብሎ እጁን ሳይታጠብ ሳይሆን አይቀርም የመጣው። የጣቶቹ ወጥ ወጥ የሚል ሽታ ምራቄን አስዋጠኝ!!
“ተከየፍሽ አይደል?... አይዞሽ… የእንቁጣጣሽ ብር ስናገኝ፣ እናጋጭና የሆቴል ቀይ ወጥ ገዝተን እንበላለን” ብሎ አጽናናኝ፡፡ እኔም እንቁጣጣሽና ቀይወጥ የሚመጡበትን ቀን በሩቁ እያየሁ ተጽናናሁ። እርግጥ ነው… ከዛ በኋላ የሆቴል ቀይ ወጥ ስበላ ሶስት ጊዜ በህልሜ አይቻለሁ፡፡
ይሄው ከስንት ጊዜ በኋላ፣ ዳዊት ቀኑን ጠብቆ መጣና የቀይ ወጥ ቀጠሯችንን አስታወሰኝ፡፡
የጣቶቹ ሽታ ውል አለኝ፡፡ የሚጣፍጥ፣ ብዙ አጥንት ያለው የሆቴል ቀይወጥ በአይኔ ላይ ዞረ፡፡ ወፍራም ምራቅ አፌን ሞላው፡፡
እነ አባባ የአክስቴን በግ አሳርደው ሳይመለሱ፣ ቀይ ወጥ በልተን ልንመጣ ተስማማን፡፡
“ግን ቀይ ወጥ ስንት ነው?” በፍጥነት እየተራመድኩ ጠየቅኩት፡፡
“እኔ እንጃ!... ወይ አምስት ብር፣ ወይ ስድስት ብር፣ ወይ…” በግምት መለሰልኝ፡፡
ብቻ ኪሴ ቀዳዳ ሆኖ ብሬን እንዳልጥለው!... ሁለት ሱሪ ማድረግ ነበረብኝ፡፡ አራት ከስልሳውን በአንዱ ሱሪዪ፣ ሶስት ብሩን በሌላኛው ሱሪዪ ኪስ አደርገው ነበር፡፡ የአንዱ ኪስ ቢጠፋ የሌላኛው ይተርፋል፡፡ አሁን ገና ገባኝ!... ቅመም ነጋዴው አባ አዘነ፣ ኬኔቴራ፣ ሸሚዝ፣ ሌላ ሸሚዝ፣ ኮት፣ ጃኬት፣ ካፖርት አድርገው ጋቢ የሚደርቡት ዝም ብለው አይደለም፡፡ ብዙ ብር ስላላቸው ነው!!
“ዴቭ…መቼም ቀይ ወጥ፣ ቢበዛ ቢበዛ ከሰባት ብር ከስልሳ አይበልጥም አይደል?...” ፈርቻለሁ፡፡
“አንተ ደግሞ!... ምን አስቦካህ?… አጋጭተን እኮ ነው እምንበላው” ኮስተር አለ፡፡
“እሱማ ነው!...” ኪሴ ቀዳዳ አለመሆኑን እየፈተሸኩ ተከተልኩት፡፡
ድልድይዋን አልፈን በታችኛው ቅያስ ስንታጠፍ፣ ድንገተኛ ስጋት ወረረኝ፡፡ ባለሁበት ቆምኩ፡፡
“የአባ ጌቴን ሆቴል ታውቀዋለህ አይደል?” አለኝ ዴቭ፡፡ መልስ ሲያጣ ዘወር ብሎ አየኝ፡፡ በፍርሃት ተውጬ ኪሴን ጨምድጄ ይዤ ቆሜያለሁ፡፡
መቼም እናቴ ባለፈው ይሄን ኪስ ጥሩ አድርጋ ሰፍታልኝ ካልሆነ ጉዴ ነው፡፡
“ምን ሆንክ?” ግራ ተጋብቶ ጠየቀኝ፡፡
“በላይኛው ቅያስ ይሻለናል፡፡ አስቻለው ካገኘን ብራችንን ይቀማናል” አልኩት፡፡
“አስቹ መታሰሩን ረሳሽው እንዴ?... አይ አንቺ ቦቅቧቃ እኮ ነሽ!” ብሎ ሳቀብኝ፡፡ ምን ማለቱ ነው እሱ?!... በስንት መከራ ያገኘሁትን ገንዘብ ተቀምቼ፣ ዜሮ እንድወጣ ይፈልጋል እንዴ?... ያውም ደግሞ ቀይ ወጥ ሳልበላ…
መንገድ ቀይረን ጉዞ ቀጠልን - ወደ ቀይ ወጥ!!
በስማም!... ብር ግን እንዴት ነው የሚጨንቀው?!... ለካ አባባ ደመወዝ የሚቀበል ቀን አምሽቶ የሚመጣው፣ አስቻለው እንዳያገኘውና ብሩን እንዳይቀማው መንገድ እየቀየረ ስለሚጓዝ ነው!
“ስማ… መንከራፈፍ የለም!... ቀልጠፍ ብለን እንገባና ሳንደናበር፣ ዘና ብለን ወንበራችን ላይ ቁጭ እንላለን፡፡ ከዛ እናጨበጭባለን፡፡ ስናጨበጭብ የሆነች ንቅሴ ሴትዮ ትመጣና ‘ምን ልታዘዝ?’ ትለናለች፡፡ ያኔ ‘ቀይወጥ’ ምናምን ብለህ መንገብገብ የለም…” አለኝ ዴቭ፣ አባ ጌቴ ሆቴል አጥር ላይ ስንደርስ ወደ ጥግ ጎተት አድርጎ፡፡
‘መንገብገብ የለም’ ይለኛል እንዴ?… የምበላው ያጣሁ መሰለው እንዴ!?... የሆቴል ቀይ ወጥ ለመቅመስ ብየ እንጂ፣ አባባ ምን የመሰለ ሙክት አርዶ፣ እማማ ምን የመሰለ ጥብስና ቀይወጥ እንደሰራች አያውቅም?!
“እና ከዛ… ንቅሴዋ ሴትዮ መጥታ ‘ምን ልታዘዝ?’ ስትለን፣ እኔ ልክ አጎቴ ከሃረር የመጣ ጊዜ እንዳደረገው፣ ዘና ብዪ ‘የሚበላ ነገር ምን ምን አላችሁ?’ እላታለሁ፡፡ ከዛ… ” እያለ ረጅም ማስጠንቀቂያና መመሪያ ይሰጠኝ ጀመር፡፡
እርሙን አንድ ቀን አጎቱን ነዝንዞ ቀምሷል መሰል፣ ‘ያለኔ የሆቴል ቀይ ወጥ የሚያውቅ ሰው የለም’ ሊል አማረው፡፡
“ተከተለኝ…” ብሎኝ ከፊት እየመራኝ ወደ ሆቴሉ ግቢ ገባን፡፡
ፊትና ኋላ በመሆን ሰፊውን ግቢ አቋርጠን ወደ ዋናው በር በመጓዝ ላይ እያለን በረንዳው ላይ አንዲት ሴትዮ ከሆነ ሰውዬ ጋር ቢራ እየጠጡ አየሁ፡፡
በስማም!... ሰውዬው… ሰውዬው… ቲቸር ጌታቸው!... ጉዴ ፈላ!
የማረገውን አጥቼ ስንቀጠቀጥ፣ ሴትዮዋ በጣም እየሳቀች ዴቭን ስታየው አየኋት፡፡
“ወይ የዘንድሮ ልጆች!... ብቻ፣ እናንተም እንትን አምሯቹህ እንዳይሆን የመጣችሁት?!” አለች፡፡
“አ… አዎ!... አምሮን ነው” ዴቭ ቆም አለና መንተባተብ ጀመረ፡፡
ሴትዮዋ በሳቅ ፍርስ አለች፡፡
“ምናባክ ነው ያማረህ አንተ ውርንጭላ?” ሰውዮው ጣልቃ ገብተው ጠየቁ፡፡
ተመስጌን!... ሰውዮው ቲቸር ጌታቸው አይደሉም!
“ቀ… ቀይ ወጥ!” አልኩ ጣልቃ ገብቼ፡፡ ዴቭ ዘወር ብሎ ገላመጠኝ፡፡
“ደሞ ለቀይ ወጥ!... እናንተን ይመራችሁ እንጂ፣ በዋጋ ከተስማማን ሁሉም ነገር ሞልቷል!” ተሞላቀቀች ሴትዮዋ፡፡ ግን እኮ እውነቷን ነው!... ዋጋ ሳንስማማ ቀይወጣችንን እንክት አርገን ከበላን በኋላ፣ ‘ሀያ ብር ክፈሉ’ ብንባል ምን ይውጠናል?!
“ግ… ግን ስንት ነው?” ፈራ ተባ እያልኩ ጠየቅኩ።
ሴትዮዋ የሚያስፈራራ ሳቅ ሳቀች፡፡ ሰውየው በንዴት አፈጠጠብን፡፡
“ተራርቆ ገበያ አለ እንዴ?... ጎራ በሉና እንነጋገራ?” አለች ሳቋን ለማፈን እየሞከረች፡፡
“እኔኮ ‘ከገባን በኋላ ነው ዋጋ የምንጠይቀው’ ብዬ ነግሬው ነበር፡፡ ዝም ብሎ ይቅለበለባል!” አለ ዴቭ ዘወር ብሎ እየገላመጠኝ፡፡ ሃፍረት ተሰማኝ፡፡
ዴቭ በልበ ሙሉነት ወደፊት መራመድ ጀመረ፡፡
“ይቺን ይወዳል መንጌ!... ገና ሳትገረዙ ሸመታ ጀመራችሁ እናንተ ጉዶች?!” ሰውየው በቁጣ ገንፍሎ ብድግ አለ፡፡ ጠረጴዛው ላይ ከተደረደሩት ጠርሙሶች አንዱን ለማንሳት ሲሞክር፣ ሴትዮዋ ጣልቃ ገብታ ከለከለችው፡፡
“ለካ እናንተን ናችሁ ገበያውን ያስወደዳችሁት!... ውርንጭላ ሁሉ!” ሰውየው አምርሯል፡፡
ሴትዮዋ ተንከትክታ ስትስቅ፣ የቢራ ጠርሙስ ተንኮትኩቶ ሲወድቅ ቆሞ ማየት አይገባም፡፡
አምልጥ!... ፊታችንን አዙረን!
አቤት ሩጫ!...ዴቭን አስከትየ ሩጫዬን ስነካው፣ በአናቴ በኩል የቢራ መክፈቻ ሽው ብሎ አለፈ፡፡
ግቢውን እንዴት እንደወጣነው፣ ዋናውን አስፋልት እንዴት እንዳቋረጥነው፣ እንዴት አምልጠን ሰፈራችን እንደደረስን፣ አባቴ ‘የታባህ ነው በአመት በዓል ስትዞር የዋልከው?’ እያለ እያገላበጠ በቀበቶ ሲገርፈኝ እንዴት እንዳለቀስኩ፣ ከኪሴ በርብሮ ያገኘውን ብር ‘ከየት አመጣኸው?’ ብሎ ሲያናዝዘኝ ምን ምላሽ እንደሰጠሁት፣ ሰባት ብር ከስልሳ ሳንቲሜን በእጄ አስይዞ ሽንት ቤት ቀዳዳ ውስጥ ሲያስጥለኝ ምን እንደተሰማኝ የማውቀው ነገር የለም!!
የማውቀው ነገር ቢኖር፣ ከዚያ ወዲህ ቀይወጥና እንቁጣጣሽ ለእኔ ጭንቀት መሆናቸውን ነው፡፡

Published in ልብ-ወለድ

“ስብሐት የጫማውን ገበር አራግፈን እንድንፈትሸው ዕድል ሰጥቶናል”
“አንድ ፀሐፊ የራሱን ጽሑፍ እንዲያሔስ ሲጠራ እኔ የመጀመሪያው ሰው ሳልሆን አልቀርም። በ‘መልክዐ ስብሐት’ መጽሐፍ ውስጥ እኔ ያቀረብኩት ጽሑፍ ብዙ እያነጋገረ ስለሆነ ለዛሬው መድረክ እንድጋበዝ ምክንያት ሆኗል፡፡ ጽሑፉን ሳዘጋጀው አምኜበትና ተጠያቂነቱን ወስጄ ነው፡፡ በፃፍኩት ጽሑፍ ላይ አልወያይም ልል አልችልም። አስተማሪው ወላጅ አምጣ እንዳለው ልጅ አባት፤ ችግሩ ምንድነው? እስቲ ሄጄ እውነቱን ሐሰቱን ልለይ ብዬ ነው የመጣሁት፡፡
“ጽሑፌ ለስብሐት የተለየ አክብሮት ያላቸው ሰዎችን ስሜት እንደጎዳ ሰምቻለሁ፡፡ ይህንን ለማዘለብና ልዩነት ካላቸው ሰዎች እማራለሁ ብዬ ብመጣም ሌሎቹ ለመምጣት ፈቃደኛ አለመሆናቸውን ሰማሁ፡፡ ተሳስቼ ከሆነ ልታረምና ልማር ነበር የመጣሁት፡፡ ተቀራርበን መወያየትን መልመድ አለብን፡፡ በግላዲያተር ፊልሞች እንደምናየው ግቡ መጠፋፋት የሆነ አካሄድ ማንንም አይጠቅምም፡፡ በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን እንደቀረበው አሽሙር፣ ስድብ፣ ስላቅና መበሻሸቁ ለውጥ አያመጣም፡፡ ሀሳብን በሀሳብ መሞገት መልመድ ይኖርብናል፡፡
“ከእኛ ውጭ የሆነን የማንንም ሀሳብ አንቀበልም የሚል አመለካከት በቡድን ከማሰብ የሚፈጠር ነው፡፡ የተለየ ሀሳብ ያቀረበ አድርባይ፣ የሕብረተሰቡ ችግር የማይገባው፣ ኦፖርቹኒስት … እየተባለ እንዲገለል ይደረጋል፡፡ የእንዲህ ዓይነቱ አካሄድ መጨረሻው ተያይዞ መውደቅ ነው፡፡ በገጠር ያደጋችሁ ሰዎች እንደምታውቁት የበጎችን ሥነ ልቦና የሚገልጽ “መናጆ” የሚባል ነገር አለ፡፡ አንድ በግ ለመሸጥ ያሰበ ገበሬ አምስቱን አብሮ እየነዳ ወደ ገበያ ይወስዳቸዋል፡፡ የምትሸጠው በግ በአገር የመጣ ነው ብላ ትሄዳለች፡፡ አራቱ ተሽጠው አንዷ ተመለሽ ብትባል እሽ አትልም፤ በአገር የመጣ ነው ብላ ተከትላ መሄዱን ትመርጣለች፡፡ በቡድን ማሰብ እንዲህ ዓይነት አደጋ አለው፡፡”
እሁድ ጳጉሜ 3 ቀን 2005 ዓ.ም ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ባዘጋጀው መድረክ የተጋበዙት አርክቴክት ሚካኤል ሽፈራው ናቸው ይህንን ንግግር በመግቢያቸው ያቀረቡት፡፡ በብሔራዊ ቤተመዛግብትና ቤተመፃሕፍት ኤጀንሲ አዳራሽ የመፃሕፍት ውይይት መድረኩ ሲካሄድ፣ ለዕለቱ የተመረጠው “መልክአ ስብሐት” በሚል ርዕስ በደራሲና ሐያሲ አለማየሁ ገላጋይ አርታዒነት የታተመው መጽሐፍ ነበር፡፡
ስብሐት ገብረእግዚአብሔርን ከሌላ ማዕዘን ማየት ለምን አስፈለገ? በሚል ወደ ዋና ርዕሰ ጉዳያቸው የገቡት አርክቴክት ሚካኤል፤ ሽፈራው አነጋጋሪ የሆነው ጽሑፋቸው የመጽሐፉ አካል ሊሆን እንዴት እንደቻለ አመለከቱ፡፡ ሁለቱ ተቀጣጥረው የተገናኙበት ጉዳይ ሌላ ነበር፡፡ አርክቴክቱ ስለ ስብሐት ገብረእግዚአብሔር ያላቸው አመለካከት የተለየ መሆኑን ያስተዋለው አርታዒው፤ ሀሳቡን እንዲጽፉት ጠየቃቸው፡፡ ይህ ከሆነ ከስምንት ወር በኋላ አነጋጋሪው ጽሑፍ የመጽሐፉ አካል ሆነ፡፡
“የስብሐትን መልካም ሰውነት፣ ጎበዝ ፀሐፊነት በ“መልክአ ስብሐት” መጽሐፍ 26 ፀሐፍት መስክረውለታል፡፡ ከእነዚህ በተለየ ብቸኛ ሆኖ በቀረበው ጽሑፌ ስብሐትን ሳይሆን አመለካከቱን ሊተች ነው የሚሞከረው፡፡ ከስብሐት አጠገብ ከነበሩ ወጣቶች አንዱ ነበርኩ፡፡ እርግጥ ነው ስብሐት ንግግር ያውቃል፣ አንደበቱም ለስላሳ ነው። ከስብሐት ጋር መከራከር ግን አይቻልም፡፡ ሁሉም ነገር መልካምና ጥሩ ነው ይላል፡፡ ይህ አመለካከትና አቋሙ ደግሞ ብዙ ወጣቶችን ለጉዳት ዳርጓል” ያሉት አርክቴክት ሚካኤል ሽፈራው፤ ሌሎች ማሳያዎችን አቅርበዋል፡፡
“ስብሐት በአመለካከቱ፣ በባሕልና ሥነ ምግባር ተጋፊነቱ አብዮተኛ ተደርጎ መወሰዱ ትክክል አይደለም፡፡ አብዮተኛ ግብ አለው፡፡ አብዮተኛ ወዳስቀመጠው ግብ ሲጓዝ ከባህል፣ ከልማድ፣ ከክልከላ … ጋር ይጋጫል፡፡ ከዚህ በተቃራኒ ዝም ብሎ ይፍረስ የሚሉ “አናርኪስቶችም” አሉ፡፡ እነዚህ ደግሞ አብዮት ሲረጋጋ አይወዱም፡፡ ስብሐት ገብረእግዚአብሔር አብዮተኛም አናርኪስትም አይደለም፡፡ በራሱ መንገድ ነው የሚኖረው፡፡ ሁሉም ነገር ትክክል ነው ይላል፡፡ ከሱ ጋር መጋጨት አይቻልም፡፡ መሰደብ ያማረው በስብሐት መሰደብ አይችልም፡፡”
ስብሐት ገብረእግዚአብሔር አመለካከቱንና የሕይወት መርሁን የቀዳባቸው ናቸው በሚል የተለያዩ ፈላስፎችን አቋም በስፋት ለማቅረብ የሞከሩት አርኪቴክት ሚካኤል ሽፈራው፤ የ“ስብሐትን ከሌላ ማዕዘን” ጽሑፍ ተጠያቂነት ምላሽ ለመስጠት ጥረዋል፡፡
የሰው ልጅ የሚኖረው ለደስታ ነው፤ ሕይወት ትርጉም የላትም፤ ሥነ ምግባር አይገዛንም፤ ጥበብን ለጥበብነቱ … የሚሉትን አመለካከቶች ይከተል የነበረ የሚመስለው ስብሐት፤ ማንንም የማስተማር ኃላፊነት የለብኝም የሚል አቋም ነበረው” ብለዋል፡፡ የፃፈልንም ሕይወቱን ነው፤ ልዩ የሚባለው “አምስት ስድስት ሰባት”ም የትግራይ ገበሬ ታሪክ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
ከተከተሉት ወጣቶች አንዳንዶቹ የስብሐት አቋምና አመለካከትን ‘አብርሆት’ ነው የሚሉ ቢኖሩም፤ ለእኔ ግን ጨለማ ነበር ያሉት አርኪቴክቱ፤ “ሳይማር ልጆቹን ለማስተማር፣ ልብስና ምግብ እንዳያጥረን ይተጋ የነበረው አባቴን መከተል ትቼ ስብሐትን ተከታይ መሆኔ ድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ጥሎኛል፡፡ ከዚህ ዓለም ለመውጣት ብዙ ኃይል ጠይቆኛል፡፡ ከሰባተኛው ሲኦል እንደመውጣት ነበር” ብለዋል፡፡
“ምስጢራዊ ባለቅኔ” በሚለው መጽሐፌ ከስብሐት በላይ የተቸሁት ፀጋዬ ገ/መድህንን ነው ያሉት አርክቴክት ሚካኤል ሽፈራው፤ ታላላቅ ሰዎቻችንን መጠየቅና መሞገት መቻል አለብን፤ ነገር ግን ይህ ዓይነቱን ሒስ ያዳበርን አይመስልም ካሉ በኋላ፤ ለ “ስብሐትን ከሌላ ማዕዘን” ጽሑፋቸው፤ አንተ ማነህ? በራስህ ሄደህ ጠፍተህ ስብሐት ምን ያድርግህ? ሰውየውንና ሥራውን ለምን ታደበላልቃለህ? … የሚሉ የማይጠቅሙ ትችቶች በተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን መቅረቡን አመልክተዋል፡፡
በ“መልክአ ስብሐት” መጽሐፍ ስብሐትን በሌላ ማዕዘን ለማሳየት የሞከረው የእኔ ጽሑፍ ብቻ ሳይሆን የካርቱን ስዕል ሰዓሊያን በሰላ አገላለጽ ስለ ስብሐት ገ/እግዚአብሔር የልባቸውን ተናግረዋል ያሉት ንግግር አቅራቢ፤ ስብሐት በጭቃ ትንንሽ ሰዎችን እየሰራ ሲለቃቸው፣ በተነፋ ፊኛ አየር ላይ ተንጠልጥሎ የሚታየው የስብሐት ምስል ጠንካራ መልዕክት አስተላላፊ ትችት መሆኑ ሲያመለክቱም “ሰዓሊ በቀለ መኮንን ጆሯችን እንጂ ዓይናችን አልሰለጠኑም እንደሚለው ልብ አላልነውም። ስዕሎቹ ግን ከባድና አነጋጋሪ ናቸው” ካሉ በኋላ ከተሰብሳቢዎች የተለያዩ አስተያየትና ጥያቄዎች ቀረቡ፡፡
የስብሐት አስተሳሰብና አመለካከት ገና ያልተደረሰበትና ወደፊትም አነጋጋሪ ሆኖ መቀጠሉ አይቀርም፡፡ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ የሚጋብዙኝ ከሆነ በስብሐትና በበአሉ ግርማ ዙሪያ ለ19 ዓመታት ያህል የሰራሁት ጥናት ስላለ አቀርብላችኋለሁ፡፡
ስብሐት በአፃፃፉ፣ በአኗኗሩ፣ በአነጋገሩ የተለየ ነበር፡፡ እሱን ማምለክ ደረጃ መደረሱ ተገቢ ነው ወይ? ሀይማኖስት ነበረው?
26ቱን ፀሐፍት የሚወክል አንድም ሰው ሳይኖር አንተ ብቻ መገኘትህ ያሳዝናል፡፡ በጽሑፋቸው ያደነቁትን በአደባባይ ወጥተው ካልመሰከሩ የስብሐት አድናቂነታቸው ምኑ ላይ ነው? የስብሐት አድናቂዎች የሚከተሉትን አቋም መሞገት ተገቢ ይመስለኛል፡፡ አንድ ሕብረተሰብ ባሕል፣ ወግ፣ ሥርዓት ባይኖረውና ሁሉም አመንዝራ፣ ጠጪ፣ ማጋጭ … ቢሆን ሕብረተሰብ ይቀጥላል ወይ? ይህ አካሄድ ሕዝብን አያጠፋም? ብዙ ያነበበ ሰው ይህንን መረዳት እንዴት ያቅተዋል? ሌላው የሒስ ባህላችን አልዳበረም በሚለው አቋምህ አልስማማም፡፡ ዘመናዊ ትምህርት ስንቀበል አላሰብንበትም እንጂ በቅኔ ትምህርት ቤት አሁንም ድረስ የሚሰራበትና ከ1500 ዓመታት በላይ ያስቆጠረ በሒስ የሚመራ ዕውቀት በአገራችን አለ፡፡
“እንደ ጥላ የገዘፉ፤ አጠገባቸው ሰው የማያስደርሱ” ብለህ ነው ንግግርህን የጀመርከው፤ አንተ የጠፋኸው ደክመው ያሳደጉህ አባትህን ትተህ ስብሐትን ለመከተል የሄድክ ዕለት ነው፡፡ ከስብሐት አመለካከት ማፈንገጥ ችያለሁ እያልክም እሱኑ ነው የምትመስለው፡፡ ከ26ቱ ፀሐፍት ብቸኛው እኔ ነኝ እያልከን ነው ያለኸው፡፡ በስብሐት ፂም ላይ ከተንጠለጠሉት ሰዎች አንዱ ነህ፡፡
የመጽሐፉ አርታዒ አለማየሁ ገላጋይ 26ቱን ፀሐፍት ወክሎ አንድ ነገር ማለት ያለበት ይመስለኛል፡፡ ሌላው፤ መልክአ መልኮች የሚፃፉት ለማነው? መልክአ ማርያም፣ መልክአ ኢየሱስ … ለቅዱሳን ነበር የሚፃፉት፡፡ የመጽሐፉ ርዕስ የተሰጠው ስብሐትንም ከቅዱሳን ጋር እንድናስበው ተፈልጎ ነው ወይ? በአሁኑ ወቅት መስመር የሳቱ፣ በምዕራባዊ አስተሳሰብ የተጠመቁ፣ ግራ የተጋቡ … ሰዎችን እናያለን፡፡ ውሉ የጠፋብን የቱ ጋ ነው? ኢትዮጵያ ሀሳቢዎቿንና አላሚዎቿን ያጣችው መቼ ነው?
“ዲሞክራሲ የመንግሥት አጀንዳ ብቻ አይደለም፡፡ ሁላችንም በየቤታችን፣ በሥራ ቦታና በተለያዩ መድረኮች ተከባብረን ለመኖርና ለመሥራት በመነጋገር የምንተማመንበት ነው ያሉት አርኪቴክት ሚካኤል ሽፈራው፤ “የእግዚአብሔርን ማንነት እየመረመርን ሰዎችን ግን ትልቅ ናቸው፣ ውስጣቸው ጥልቅ ነገር አለ በሚል እንደ ጣኦት መመልከታችን ተገቢ አይደለም” ብለዋል፡፡
“ክርክር፣ ሙግትና ውይይታችን የሚያስገኘው የተሻለ ሦስተኛ ሀሳብ ካለ አምነን መቀበልን መልመድ አለብን፡ እነ ፕሌቶን በጽሑፋቸው ስናውቃቸው የአክሱማዊያን ዘመን ፈላስፎቻችንን አናውቃቸውም፡፡ ክፍተት መተው እንዲህ ዓይነት ጉዳት ያስከትላል፡፡ ትህትና የሌላቸው ትላልቅ ሰዎች ሌላውን ዝቅ አድርገው ይመለከታሉ፡፡ እንደነዚህ ዓይነት ታላላቆቻችንን መሞገት መልመድ አለብን፡፡
“ስብሐትን አትንኩት” የሚሉ ሰዎችን ሀሳብ አከብራለሁ፡፡ ለምን መነካት እንደሌለበት ግን ሊያስረዱን ይገባል፡፡ “እነ እከሌ ቤት ቢሆን ማን ያስገባህ ነበር?” የሚሉኝ ይኖራሉ፡፡ እውነት ነው ስብሐት እንድናውቀው፣ በሱ ዙሪያ እንድንነጋገር በሩን ከፍቶልናል፡፡ ስብሐት ባለው ዝነኛነት እሱን በመቃወም መፃፃፍም ሆነ መድረክ ላይ መውጣት ያስፈራል፡፡ ለተጠያቂነት ዝግጁ የሆንኩት በጎውን ወስደን የማይጠቅመውን እናርም በማለት ነው፡፡ ዛሬ ቤተሰብ እየመራሁ ነው፡፡ እኔን አርአያው አድርጎ የሚከተለኝ ልጅ አለኝ፡፡ እዚህ ደረጃ መድረስ ቀላል ነገር አልነበረም፡፡ መጠየቅና መጠየቅ ስጀምር ነው መሠረት መያዝ የቻልኩት” በማለት ሲያጠቃልሉ ደራሲና ሐያሲ አለማየሁ ገላጋይ ማጠቃለያ ሀሳብ አቀረበ፡፡
“መጽሐፉን ለማሳተም ያሰብኩት ስብሐት በሕይወት እያለ ነበር፡፡ ስብሐት አንብቦት አስተያየት ሰጥቶበት ነበር፡፡ የቀድሞውን ትውልድ መንካት ከባድ ነው፡፡ ግን መለመድ አለበት፡፡ “መልክአ ስብሐት” የትውልዱ መልክ ነው፡፡ እኔ ከስብሐት ጋር ተዋውቄ በራሴ መንገድ መሄድ ችያለሁ፡፡ ስብሐት የሁሉንም ሰው አመለካከትና አካሄድ ያከብራል፡፡ የጫማውን ገበር አራግፈን እንድንፈትሸውም ዕድል ሰጥቶናል፡፡”

Published in ጥበብ

“The Old Man and The Sea” የገናናው አሜሪካዊ ደራሲ ኸርነስት ሄሚንግዌይ ዝነኛ ስራ ነው፡፡ አንብበን ተደንቀን በልባችን የያዝነው እንዳለ ሆኖ፣ የዘመነኞቹን ሀያሲያን አንጀት አርስ ውዳሴም አድምጠናል፡፡
“ከጽሁፉ አንድ ቃል ቢወጣ ወይም ቢቀየር ኖሮ፣ ጠቅላላ ድርሰቱ ሌላ መልክ ይኖረው ነበር!”
በእኛ የቅርቡ የስነ-ጽሁፍ ዓለም ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ከልቤ ይሄንን ያሰኘኝ የበዕውቀቱ ስዩም “እንቅልፍ እና ዕድሜ” ነበር፡፡ ብዙ ሃሳብ በተጫነባቸው ቃላት እና አረፍተ ነገሮች የተገነባ ህያው ልብ ወለድ!
ጊዜ አለፈ፡፡ ቀጥሎ በመጡት ዓመታት በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ስር ከሚወጡ ማለፍያ ሳምንታዊ ጽሁፎች መካከል “አለማየሁ ገላጋይ” በተሰኘ ስም የሚቀርቡ መጣጥፎች ልቤን ይገዙት ጀመር፡፡ ደፋር፣ ምሉዕ እና ጥልቅ ትንታኔዎች፡፡ ማነው ይህ ሰው? የዘወትር ጥያቄዬ ሆነ፡፡ በራሱ ምን ሰርቷል? ስራዎቹ ምን ያህል ናቸው? ምንስ አቅም አላቸው? …

እነሆ አለማየሁ!
ከዕለታት በአንዱ፣ እንዲሁ በአጋጣሚ፣ እኔ እና አለማየሁ ተገናኘን፡፡ ያገኘሁት ሰውየውን ሳይሆን የበኩር ስራውን “አጥቢያ”ን ነበር፡፡ አራት ኪሎ፣ ዩኒቨርሳል መጽሃፍት መደብር ውስጥ፡፡ አየሁ የቃላት ተዓምር በ”አጥቢያ”፡፡ ሰማሁ ክሱት ትንቢት ከ”አጥቢያ”፡፡ በቃ፣ አለማየሁ የቀን ተቀን የወሬ ርዕሳችን ሌላ ቀለም፣ ሌላ አጀንዳ ሆነ፤ ለእኔ እና ለጓደኞቼ፡፡ ይህ ሰው ማን ነው? ሌላ የተራ አንባቢ ጥያቄ፡፡ የት ተወለደ? ምን ተማረ? መቼ? እንዴት? እስከ ወዲያኛው መልስ አልባ ጥያቄዎች፡፡ በከፊልም ከሰውየው ጋራ ያስተዋወቀን የታሪክ ተመራማሪው ብርሃኑ ደቦጭ ነበር … ሊያውም በጣም በቅርብ፡፡
በግሌ የእርሱን ስራዎች ከሌሎች ከምወዳቸው ጸሃፊዎች ስራዎች ጋር የማነፍነፍ ያህል ማሰስ ተያያዝኩ፡፡ ከአዲሱ ሚሊኒየማችን ማግስት ጀምሮ ድንቃ ድንቅ የልቦለድ ስራዎቹን “ቅበላ”ን እና “ኩርቢት”ን፣ ጥልቅ ሂሳዊ ፍተሻውን “ስብሃት ገ/እግዚአብሔር ህይወትና ክህሎት”ን፣ ፍልስፍና ነክ የትርጉም ስራውን “የፍልስፍና አጽናፍ”ን፣ እና ወቅታዊ ፖለቲካዊ፣ ታሪካዊና ማህበራዊ ዳሰሳውን ያቀረበበትን “ኢህአዴግን እከስሳለሁ!” እንዲሁም በዚሁ ክረምት በአርትኦትና መለስተኛ ጽሁፍ በማዋጣት የተሳተፈበትን “መልክዓ ስብሃት”ን በተከታታይ አቀረበልን፡፡ አስገራሚ ትጋት ነው። በጠቅላላ ስራዎቹ እጅግ በጣም ድንቅ የሚሰኙ ናቸው፡፡ ሰውየው ሰፊ ንባብ እንዳለው ያስታውቃል።

የብርሃን ፈለጎች
ይህ የአለማየሁ ገላጋይ ሌላው ትንግርታዊ ልብወለድ ነው፡፡ እንደ አዲስ ዓመት ውድ ስጦታ የቆጠርንለት፡፡ ያው ያ ምትሃታዊ የስነ ጽሁፍ ክህሎቱ እንዳለ ነው፡፡ ወትሮም የምናውቅለት አስደናቂ ቃላት አጠቃቀሙ፣ ውብ ገለጻዎች፣ ማራኪ የገጸ-ባህሪ አሳሳሉ እመርታ ታይቶባቸዋል፡፡ ጭብጡም እግዚኦ! የሚያሰኝ ምጥቀት ይዟል፡፡
በሁለት ክፍል የተሰደሩት ውብ ታሪኮች ልጅነት እና ጉርምስናን ጠልቀው ገብተው ይመረምራሉ፡፡ ልጅነት፣ በክፍል አንድ “የግንፍሌ ማለዶች” ስር፣ ጉርምስና፣ በክፍል ሁለት “የሞጆ ቀትሮች” ስር ቀርበዋል፡፡ አሁን አሁን እየተለመዱ እንደመጡት፣ በበርካታ ጸሃፊያን እንደሚቀርቡት፣ የልጅነት ወጎች እዚያው ልጅነት ላይ ተቀንብቦ አለመቅረቱ፣ በተራኪው “መክብብ” ህይወት ውስጥ የጉርምስናን ምስቅልቅል የሽግግር ወቅቶች ለማሳየት መጣሩ፣ ለነባራዊ ደቃቅ መሳይ ክስተቶች ጭምር ስውር ምክንያትና ውጤት ለማቅረብ መትጋቱ፣ በተለይ ባብዛኛው ጸሃፊያን ዘንድ እንደመዘንጋት በተባሉት ከ13 እስከ 18 ዓመት ዕድሜ ክልል ውስጥ (የጉርምስና ዓመታት) ራስን ለአንዴ እና ለመጨረሻ ለመቅረፅ ከቤተሰብ-ማህበረሰብ አንስቶ እስከ እግዜር ድረስ የሚዘልቅ ውስጣዊም ውጪያዊም ግጭት፣ በትናንት እና በነገ መሃል (በልጅነትና በአዋቂነት መንታ መንገድ) መሰፋት እና መወጠር እና የመሳሰሉት ቁምነገሮች ልቦለዱ የመረመራቸው የተዘነጉ እውነታዎች ናቸው፡፡
የመጀመሪያው ክፍል ሌጣ አጫጭር 14፣ ሁለተኛው 22 ባለ ርእስ ምዕራፎችን አካተዋል፡፡ የልቦለዱ ማሰሪያ ቁልፍ ድህረ ታሪኩ ነው፡፡ በዋዛ እንዳይታለፍ!!!

አዳም እና አለማየሁ
ሃያሲ አብደላ እዝራ “ስለ መጽሐፉ” አስተያየት ሲሰጥ “የአዳም ረታ በጐ መንፈስ ያረፈበት አብይ ልብ ወለድ” ይለዋል፡፡ እውነትም ታዲያ “ኩርቢት” እና ይሄ “የብርሃን ፈለጐች” በአዳም ረታ ስም እንኳ ቢታተሙ ያለማወላወል የምንቀበላቸው አይነት ናቸው፡፡ ልጅነት ላይ ማተኮራቸው፣ የተቡ ቃላት መጠቀማቸው፣ ስውርነታቸው እና እጅግ ጥልቅ እይታዎቻቸው መሳ ለመሳ የሚያቆማቸው የወል ገንዘባቸው ነው፡፡ በ”ግራጫ ቃጭሎች”፣ በ”ትርንጐና ገብረ ጉንዳን” ያስተዋልነው የአዳም ሃይል ከላይ በጠቀስናቸው የአለማየሁ ስራዎች ውስጥ ተደግመዋል፡፡ በእርግጥ ለእኔ አለማየሁ ጉልበቱ የተገራ አዳም ሆኖብኛል፡፡ በአዳም “ትንቢተ ቁራ” ውስጥ እንደምናየው ያለ በቅንፍ ውስጥ ገብቶ ሶስት እና አራት ገጾች ገለጻ መስጠትን የመሰለ የጉልበት ብክነት በ “የብርሃን ፈለጐች” ውስጥ ከቶም የለም። እዚህ የተሻለ ፍጥነት አለ፡፡ “የብርሃን ፈለጐች”ን አንድ አንቀጽ ሳያነቡ ማለፍ “የጠፋውን እግዜር” እንደሚያስሰው ባካኝ “ቱሪስት” መነሻ እና መድረሻ የማጣት ያህል ነው፡፡ ያለነገር የተደነቆለ ቃል እና ሃረግ የለም፡፡ ብርሃማነቱ ሳይጐድልበት፡፡ “ፀኸየች” የሚል ውብ ቃል ያነበብነው እዚህ ነው፡፡ ለዚህ ነው ኸርነስት ሄሚንግዌይት ቀድመን ያነሳነው፡፡

ፍሩድ እና አለማየሁ
ይሄ አለማየሁ የስነ ልቦና ሊቅ መሆን አለበት። ልቦለዶቹ ባብዛኛው የግለሰብ እና የማህበረሰብ ስብእናን በግል እና በጋራ በርትተው የሚፈትሹ ድንቅ የስነ ልቦና ምርምር ውጤቶች ናቸው፡፡ ከ“አጥቢያ” አንስቶ፣ “ቅበላ”ን ጨምሮ የታየው ይኸው እውነት በ”የብርሃን ፈለጐች” አድጐ፣ ጐልብቶ እና ተራቅቆ ቀርቦልናል፡፡
ቤተሰባዊ የአስተዳደግ ባህላችን፣ የልጅነት ገጠመኞቻችን፣ የወዳጅ ዘመድና ማህበረሰባዊ ጉድኝቶቻችን በስብዕና ግንባታ አንጻር የሚያበረክቱልንን በጐም ሆነ እኩይ አስተዋጽኦ ብቻም ሳይሆን በምናየው እና በማናየው ዓለም መካከል ያለውን ጽኑ ትስስር፣ በምንረዳው እና በማንረዳው የአእምሮአችን አሰራር እና ውጤት፣ በህልም እና በእውን አለም መካከል በተዘረጋው ስስ ድንበር ላይ የሚያጠነጥኑ ጠንካራ ታሪኮችን ከለስላሳው “የብርሃን ፈለጐች” ፈልቅቆ ማውጣት ይቻላል፡፡ ጠጣሩ የሲግመንድ ፍሩድ የPsychoanalysis (በማናዘዝ የአእምሮ እረፍት የማምጣት) ልምምድ ሁላ በልቦለዱ ቃለ ምልልሶች ውስጥ ይስተዋላል፡፡
እግዜር እና አለማየሁ
ከArts for Arts Sake በተጻራሪው እንደ እንግሊዛዊው በርናንድ ሾው፤ ማህበረሰብ ለማነጽ የሚታትሩ ፀሐፊያን በየአገሩ በብዛት አሉ፡፡ በዚሁ በእኛው አገር በዚሁ በእኛው ዘመን እንኳ በልብ ወለዶቻቸው ብቻም ሳይሆን በተለያዩ የመጣጥፍ ስራዎቻቸው ሞራልን የሚሰባብኩ አያሌ ናቸው፡፡ ዘነበ ወላን፣ ዳንኤል ክብረትን፣ ኤፍሬም ስዩምን፣ እንዳለ ጌታ ከበደን እና በግልጽ “ገጣሚ ለዘመዶቹ/ለሰው ልጆች” እንደሚቆረቆር የነገረንን ተወዳጁ በዕውቀቱ ስዩምን ጨምሮ ሌሎችንም ማንሳት ይቻላል፡፡ ስብከቱ አይጩህ እንጂ አስተሳሰቡ የሚያስማማ ነው፡፡
ለእኔ አለማየሁ ገላጋይ በእዚህ በ “የብርሃን ፈለጐች” ልብወለዱ እኔን መሰል በጐና ክፉ እግዜር አልባዎችን ተዋግቷል፣ ፈንክቷል፡፡ “እግዜር ጠፍቷል” በሚል ቁንጽል እና ወላዋይ “የፍልስፍና እውቀት” ሰበብ ስርዓት አልበኝነት ሲያቆጠቁጥ፣ ፈሪአ እግዚአብሔር ጠፍቶ ማን አለብኝነት ሲያገነግን ውስጥ ውስጡን ሰብኳል፡፡ በፍትሃዊ ዳኛ፣ በአገናዛቢ ታዛቢ አልባነት ሰው የራሱን ፍርድ ለመስጠት ሲነሳ፣ በልብ ወለዱ የተፈጠረችው መጠነኛ ዓለም ወደ መፍረስ ስታዘነብል አሳይቷል። “ቱሪስት” እንደመጣባት እንግዳ ምድር ከጨረቃ ባሻገር በሌለ ቀጣይ ህይወት አልባነት ሃሳብ ንውዘት ለእብደት ሲያቆበቁብ፣ እንደ “መክብብነቱ” የህይወት ዘበትነት ሲገዳደረው፣ የህልም እና የእውን አለም ድንበር ሲደረመስበት ተስተውሏል፡፡ ስነ ጽሑፋዊ ይዘቱ ስለገነነ፣ ስብከቱ ፈጽሞ ስለተሰወረ፣ ጣዕምናው በጣም ሆነ፡፡ እኒህን መሰል የእጅ አዙር ምስክርነቶች ብቻ ሳይሆኑ፣ የቅዱስ መጽሐፋት ታዋቂ ህግጋት በሰው ልጅ ተሽረው የሚያስከትሉት ቀውስ ያው እንደዝምዝማት በስውር ስፌት ቀርበዋል፡፡ “ባል የሚስቱ ራስ ነው” የሚል ቃል ታጥፎ ቤት ሲናድ፣ “አታመንዝር” ቸል ተብሎ የፍልሚያ እና የሞት ሰበብ ሲሆን ተተርኳል፡፡ እጅግ ያምራል!
ሌላም በጉልህ ያስደነቀኝ የስነ ጥበብን ግብ የማጉላት ስራ አሽትቼአለሁ፡፡ ቀደም ብለን የጠቃቀስናቸው ዘላለማዊ እሴቶች በጽሑፍ ኪን መቅረባቸው እንዳለ ሆኖ፣ የተሰወረን እግዜር (በአባት ተመስሎ የጠፋን) በስነ ስዕል ሃይል የማግኘት ተአምር! ለስዕሉም መነሻ ሙዚቃ መሆኑ! ብራቮ አለማየሁ!

ድንቅ ገለጻዎች
“ማናሉን በፍርሃት አየኋት፡፡…የእናቷ አይነት ደቃቅ አበባ የተበተነበት ቀሚስ ለብሳለች፡፡ በቆዳ ጫማ ሞድ የተሰራ አጭበርባሪ ኮንጐ አድርጋለች።…” (ገጽ 44)
“ወሬ ተሸሽቶ የትም አይደረስ፤ … ወሬ ታግሎ የሚጥልህ መኖሩን በሙሉ ትኩረት ስታረጋግጥለት ብቻ ነው” (ገጽ 68)
“ይሄን አስቀያሚ ዓለም የማሻሻል ፍላጎቴን በህልሜ ለማሟላት ወደ እንቅልፍ አለም የገባሁ ይመስለኛል … (ገጽ 70)
“አባቴ በእምምታ “ናፍቆቴ”ን እየተጫወተ ጊታሩን ማጀብ ጀመረ፡፡ … ጨርሶ ለመጥለቅ አፍታ የቀራት ጀንበር ይኽ ነው የማይባል ደስ የሚል ቀለም አንሰራፍታለች፡፡ እነ ጋሙዳው አመል ሆኖባቸው እንደኩርሲው ሁሉ በመስኩም ይጋፋሉ፡፡ ንጹህ ፊት ላይ የሚታየው ተመስጦ እንደ ጀምበሯ ቀለም ይህ ነው የማይባል አይነት ነው፡፡ ሀዘን ቅልቅል ደስታ፡፡ እግሮቿን ወደ ጎን ሸርመም አድርጋ ጉልበቷን በማነባበር ያለችበትን ልብ ሳትል ተቀመጠች፡፡ እኔ አጠገቧ ሆኜ ቀረሁ፡፡ ይህ ሁኔታና ምስል የረጅም ዘመን ቅርሴ ሆኖ በህልምና በእውን ቅልቅልነት አብሮኝ ኖሯል፡፡ የልጅነት ጊዜዎቼ ሁሉ በእዚች ዕለት ሁኔታ ተተክቶ የግሩም ዘመን ናፍቆትና ተነጥሎ የመቅረት ብሶት ተቀላቅሎ አሁንም ልቤን ይጎበኘዋል። … ነገሮች ሁሉ እዚች ቦታና ዕለት ላይ መቋጫ አጥተው እንደተገተሩ ወደ ዘላለማዊ ምስልነት ቢቀየሩ ኖሮ እያልኩ ብዙ ጊዜ ተመኝቻለሁ። … (ገጽ 72)
“ከድብድቤ ውጤት ጋር በተለየ መልኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ተዋወቅሁ ማለት እችላለሁ፡፡ በጥቃት፣ በእልህ፣ በቁጭት፣ በበቀል የምናካሂደው ድብድብ ውጤቱን ክብር ስንለው በወዲያ በኩል ውርደት ሊሆን እንደሚችል ተገለጸልኝ፡፡ ከንዳዴ ጋር የገጠምኩት አንሼ መታየትን በመጥላት ቢሆንም አሸንፌም ከትንሽነት እንዳልወጣሁ እዚህ ቆሜ ገባኝ፡፡ … (ገጽ 117)
“ከንግግር ውጭ ያለ መግባቢያ ሁሉ መጠፋፊያ እንደሆነ አውቃለሁ፡፡” (ገጽ 124)
“ፍርድ ሁሉ የሰው እንጂ የእግዚአብሔር እንዳልሆነ እንዴት ሳላውቅ ቆየሁ? …” (ገጽ 176)
“የቴክኒክ መቋረጦች”
ትየባ ላይ የተፈጠሩ እዚህ ግቡ የማይባሉ ህጸጾችም ሳይኖሩት አልቀሩም መጽሃፉ፡፡ እስካሁንም እንደተስተዋሉ እናምናለን በደራሲው። ሁለተኛው እትም ላይ የሚታረሙ የቃላት ድግግሞሾች፣ የተዛነፉ ስርዓተ ነጥቦች፣ የተገደፉ ሆሄያት፣ የተዘባረቁ ፊደላት አሉ፡፡
ሌላም በገጽ 213 ከሌሎች ጋር መምጣቷ የተገለጸው “ምዕራፍ” በገጽ 216 “ዛሬ መጥታ አለመጠየቋ ሌላ ምልክት ሆነኝ፡፡” ተብሏል፡፡
በመጨረሻም
ይሄ ጽሁፍ የተሰናዳው በዚህ ዘመን በሰበብ አስባቡ ያጣነውን፣ “የብርሃን ፈለጎች” ከብርሃን ጋር የለገሰንን፣ እንደአደይ አበባ የሚያፈካ ደስታ፣ አንብባችሁ ታጣጥሙ ዘንድ ለመጋበዝ ነው። እግረ መንገዳችንን መልካም አዲስ ዓመት እንመኛለን፡፡
ረዥም ዕድሜ ለአለማየሁ!!

Published in ጥበብ
Monday, 16 September 2013 08:21

ጥበብ (ዘ -ፍጥረት)

ጥሩ የጥበብ ፈጠራ ምን አይነት ነው? መካሪ ነው፤ ዘካሪ፣ አስተማሪ፣ ህይወትን የሚያሳይ መነጽር ነው፡፡ እነዚህ ሁሉ የዋህ አስተያየቶች ናቸው፡፡ ምንድነው የዳንስ ትርጉም?...ሰው ሲደንስ ተደስቶ ነው ለማለት አይቻልም፡፡ በለቅሶም ሙሾ ሲያወጣ ይጨፍራል፡፡ ደረቱን እየመታ፡፡ ለዚህ ነው ለውበት ሀሊዮት ልናገኝ የማንችለው፡፡ ታሪክ ለመዘከር ጥበብ ያስፈልገዋል፡፡ ጥበብ ላይ ነፍስ ለመዝራት ግን ታሪክ አያስፈልገውም፡፡
የፈረንሳይ ቋንቋ ትርጉሙ ምንድን ነው? እንደማለት ይሆንብናል፡፡ የፈረንሳይኛን ቋንቋ ወደ አማርኛ እናስተረጉማለን እንጂ…የፈረንሳይኛ እና የአማርኛ ቋንቋ ምንድነው ትርጉማቸው ልንል አንችልም፡፡ የሃሳብ ቁመት ስንት ነው ብሎ ከመጠየቅ የተለየ ስላልሆነ፡፡
                                                   * * *
ጥበብ ከራሱ በስተቀር ሌላ ትርጉም የለውም። ብቸኛ ነው፡፡ ጥበብ የተለምዶውን የህይወት፣ የማህበረሰብ የቀድሞ ትርጉም አይቀበልም። ደራሲውን፣ ገጣሚውን፣ ሰአሊውን በማወቅ ከጠቢቡ አኗኗር በመነሳት፣ ጥበቡን መተርጐምም አይቻልም፡፡ የሰውየው ስነልቦና የጥበብን ስነልቦና ለማጥናት አይጠቅምም፡፡
ቫንጐ ያረጁ ጥንድ ጫማዎች ስሏል፡፡ ምንም አዲስ ነገር አልነበራቸውም አሮጌዎቹ ጫማዎች በስዕል ላይ እስኪቀርቡ ድረስ፡፡ Defamiliarization የጥበብ መንገድ ነው፡፡ (በብረት የተሰራ ሃውልት ከተሰራበት ጊዜ አንስቶ ብረት አይደለም፡፡ ከብረቱ ቀድሞ የሚጠራው “የብረት ምን?” የሚለው ነገር ነው፡፡) ከተለመደው ውስጥ ያልተለመደውን ማግኘት፡፡ ነገርዬው ከሚኖርበት አለም ነጥለን ስንገልፀው፣ በሱ ዙሪያ አዲስ ጥቅል የእውነታ ማስተሳሰሪያ በሰው ግንዛቤ ውስጥ ይፈጠራል፡፡
ከጐዶሎው ውስጥ ሙሉነት (holistic) በተሻጋሪ ከፍታ (transcendental aspect) ይወለዳል፡፡ የተወለደ ልጅ ምንድነው ትርጉሙ፣ ሲያድግ ምን ይሆናል፣ የተወለደበት አላማ ምንድነው? የወለደውን አባቱን ለምን አይመስልም? ለማለት አይቻልም፡፡ አባቱን ካልመሰለ “ውሸት ነው” ብላ ህልውና በራሷ እጅ አታጠፋውም፡፡ ተፈጥሮ ውበት ኖሯት ትርጉም ላይኖራት እንደሚችለው ፈጠራም ይሄንኑ ተከታይ ናት፡፡
ለጥበብ ፈጠራው ትልቅነት መሰረቱ ፈጠራው ራሱ እንጂ ፈጣሪው አይደለም፡፡ ግጥሙ ባይኖር ገጣሚው ገጣሚ ባልተባለ ነበር፡፡ በሆነ ምክንያት ጥበቡ ሳይፈጠር ቢቀር ኖሮ፣ ስለ ስራውም ሆነ ስለ ሰሪው መመራመር፣ መጠየቅ አይቻልም ነበር። ስሪቱ የሰሪው እና የስሪቱ ቅንጅት ቢሆንም…ውጤቱ ከድምሩ በፊት ከነበሩ ማንነቶች በላይ ነው፡፡ ስለመነሻው በማጥናት መድረሻውን ማወቅ ወይንም መስራት በውበት እውነታ አይቻልም፡፡ መነሻውም መድረሻውም ውበቱ ነው፡፡ Its an end in itself.
ከመድረሻው ውስጥ ሌላ መድረሻ ሊፈጠር አይችልም፡፡ ጥበቡ ራሱን በራሱ አያበዛም፡፡ በተመልካቹ ስሜት ውስጥ ግን ሃሳብን ሊያበዛለት ይችል ይሆናል፡፡
The work is to be released the artist into pure self-subsistence. It is precisely in great art that the artist remains inconsequential as compared with the work, almost like a passage way that destroys itself in the creative process for the work to emerge.
ስራው (ጥበቡ) በራሱ የመናገር ነፃነት አቅም ካልተሰጠው ውበት ደረጃ አይደርስም፡፡ ምን ማለት እንዳለበት አስቀድሞ የሚያውቅ ገጣሚ ውበትን ሳይሆን ስብከትን ነው የሚያበረክተው፡፡ ስብከቱ ለህይወት እንጂ ለጥበብ እውነታ ምንም የሚፈጥረው አዲስ ነገር አይኖረውም፡፡
Inspiration ጥበብ በራሱ አንደበት ስንፈቅድለት የሚከሰት ነገር ነው፡፡ ምን እንደሚናገር አስቀድመን ልናውቀው አንችል፡፡ “How do I know what I think until I see what I say” እንዲል ደራሲው E.M Forester. አርቲስቱ የተገለፀለትን የሚከተል ነው፡፡ መገለጥ ከሌለ አርቲስቱም አርቱም የለም። ህይወት እና ሞት በሌሉበት ትንሳኤ” ሊታሰብ አይችልም፡፡ ጥበብ ከሰው ልጅ ህይወት እና ሞት ውስጥ የሚወለድ ትንሳኤ ነው፡፡
የመገለጥ ብርሃን የመግለጫ መንገዱን Style አብሮ ስለሚሠራ ይዘትና ቅርጽን በጥበቡ ላይ ለያይቶ መገንዘብ አይችልም፡፡
The power of disclosure itself is not our own it is not a human creation- the artist can compose only what of itself gathers together and composes itself.
የፈጠራ የጥበቡ ባለቤት በዚህ ረገድ ጥበበኛው አይደለም፡፡ የውሃው ባለቤት ምንጩም የፈሰሰበት ቧንቧም እንዳልሆኑት፡፡
የተፈጠረው ጥበብ ውበት የሚሆነው ብቸኛ (Singular) መሆኑ ላይ ነው፡፡ አርቲስቱንም፣ ተፈጥሮንም፣ ህይወትንም አለመምሰሉ ላይ፡፡ አለመምሰሉ፤ ልዩ እና ብቸኛ ያደርገዋል፡፡ ለምሳሌ አካፋ፤ የፈለገ ልዩ እና በአዲስ መንገድ በአዲስ ፋብሪካ ወይንም ቅርጽ የተሰራ ቢሆን እንኳን ፍጡርነቱን ከግልጋሎቱ መነጣጠል አይቻልም፡፡ አካፋን አካፋ ወይንም ማንኪያ ብለን ብንጠራው የሆነ ነገር ከማፈስ ወይንም ከማማሰል ውጭ ጥቅም ሊኖረው አይችልም፡፡ የራሱ ለራሱ የሆነ ጥቅም ማለቴ ነው፡፡
“the work of art is similar rather to the more thing which has taken shape by itself and is self contained.
በድንጋይ የታነፀ ቤት፣ ሁለት ነገሮችን በአንድ ላይ ጠቅልሎ የያዘ ነው፡፡ ድንጋይ እና ቤት ነው፡፡ ድንጋዩ ከተራራ ተፈንቅሎ የመጣ ሊሆን ይችላል። ተራራው፤ የተፈጥሮ መወኪያ (representation) መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ቤት ግን፤ ተፈጥሮ ውስጥ የምናገኘው ነገር አይደለም፡፡ በተጨባጩ ውጫዊ እውነታ ላይ ቤትን የሆነ ወይንም የሚመስል ነገር የለም፡፡
በ“World” እና “earth” መሀል ያለ ግንኙነት በሰው አማካኝነት የተቋጠረ ነው፡፡ በተጨባጭ የሚዳሰሰው፣ የሚታየው፣ የሚለካው እና የሚመዘነው ነገር “Earth” ነው (“አፈር” ማለት ነው ሀሌታ ትርጉሙ)፡፡ አፈሩ በሰው ምክንያት “አለም” ይሆናል፡፡ ድንጋዩ በሰው ምክንያት “ቤት” ወይንም ህንፃ እንደሆነው፡፡ የአካፋ እና የማንኪያ ግልጋሎትም ሆነ ትርጉም ሰው እስካለ ድረስ ብቻ እውነት ይሆናል፡፡ ለራሳቸው እንደራሳቸው ምንም ትርጉም የላቸውም፡፡
ጥበብ ግን ከዚህም ደረጃ በጥቂቱም ቢሆን ከፍ ያለ ነው፡፡ ለራሱ እንደራሱ…በሰው ልጅ አሊያም ከተፈጥሮ ምክንያትም ሆነ ትርጉም ሳይቀዳ ህልውና አለው፡፡ ከድንጋዩ የታነፀው ቤት በሰው አማካኝነት ሲፈጠር…በመፈጠሩ ድንጋዩን እንዲጠፋ ወይንም ህልውናውን እንዲያጣ አያደርገውም፡፡
እንዲያውም፤ በአፈር ቋንቋ ይመዘን፣ ይሰፈር፣ ይገለጽ የነበረውን objectivityወደ ሌላ ባለ (subjective) እውነት ከአፈሩ ውስጥ ይፈጥረዋል፡፡ ይህም ፈጠራ ትርጉም ካለው ለሰው እንጂ ለተፈጥሮ/እግዜር አይደለም፡፡ (አዳም መጀመሪያ አፈር ነበር/በመጨረሻ ወደ አፈር ቢመለስም አይገርምም፡፡ ነገር ግን በፈጣሪው አማካኝነት በተሰጠው ትንፋሽ ፍጡር ወይንም ሰው ሆነ፡፡ ወደ ቀድሞው መሰረቱ ቢመለስ እንኳን ከቅድመ ሞቱ በፊት የነበረው ማንነቱ፣ ከሞቱ በኋላ ያለውን አይመስልም፡፡ ድሮ አፈር ከነበረ ወደ አፈር ተመልሶ ከመግባቱ በፊት ግን ሰው ነበር፡፡ የተፈጠረ ነገር ቢጠፋ እንኳን ተከውኖ እንደነበር ግን መካድ አይቻልም፡፡ የደራሲው ፈጠራ ከመዛግብት ላይ ቢፋቅ እንኳን ፈጠራው መወለዱ ሊፋቅ አይችልም፡፡
“እኔ ጨረቃን ሳሳየው እሱ ጣቴን ያያል” እንደሚለው ብሂል፤ ቤቱን ሳሳየው ቤቱ የተገነባበትን ድንጋይ የሚያይ ሰው፤ ውበትን ወደ ተራ ማንነቱ (አፈር) ለመቀየር ስለፈለገ ነው፡፡ ቤቱን ሳሳየው የቤቱን የፈጠራ ውበት እንደመነሻና መድረሻው (an end in itself) መገንዘብ ያልቻለ መስተሀልይ፣ ለውበት እውቀት ዝግጁ አይደለም፡፡
የግጥሙ፣ የድርሰቱ፣ የስዕሉ ትርጉም ግጥሙ፣ ድርሰቱ፣ ስዕሉ ራሱ ነው፡፡ ሰለሞን ደሬሳ እንደሚለው፤ ግጥሙ እንደአጋጣሚ የተለያዩ የህይወት ትርጉሞችን ተንተርሶ ሊገኝ ይችላል። ሰባኪ፣ አስተማሪ፣ አራሚ ሊሆን ይችላል። በድንጋይ የተሰራ ቤት የድንጋይ ባህሪዎችን ተላብሶ እንደሚገኘው፡፡ በብረት የተሰራ ሀውልት የብረት ባህሪዎችን በተጨባጩ (ሳይንሳዊ) ልኬት እንደሚንተራሰው፡፡ ሰው እንደ እንስሳት አለም ስጋን ይለብሳል፡፡ ግን ከለበሰው ስጋ በላይ የሚያስብ ፍጡር ነው፡፡ ሃሳቡን በንግግር መግለጽ ይችላል፡፡

Published in ጥበብ

በናፖሊዮን ሂል የተፃፈው “The 17 principles of success” የተሰኘ የስኬት መርሆዎችን የያዘ መፅሃፍ “17ቱ የስኬታማ ህይወት ምስጢራት” በሚል በፋንታሁን ሃይሌ ተርጓሚነትና በእስክንድር ስዩም አርታኢነት ለንባብ በቅቷል፡፡
ተርጓሚው በመፅሃፉ መቅድም ላይ ባሰፈረው መልዕክት “የዚህ መፅሃፍ አንባቢ ስኬታማ መሆንን አጥብቆ ይሻ እንደሆነ ለዚህ የናፖሊዮን ሂል መፅሃፍ ትኩረት ሊሰጥ ይገባል፡፡ በዚህ መፅሃፍ ውስጥ የተብራሩት የስኬት መርሆዎች አንባቢ እንዴት ሊረዳቸውና በህይወቱ ውስጥ ተግባራዊ ሊያደርጋቸው እንደሚችል የሚጠቁሙ ጭምር ናቸው” ብሏል፡፡
17ቱ የስኬት መርሆዎች በሚል ከተገለፁት ውስጥ የዓላማ ቁርጠኝነትን ማዳበር፣ ውጤታማ ህብረት መፍጠር፣ አስደሳች ስብዕናን መገንባት፣ በትክክል ማሰብ ወዘተ የሚሉት ይገኙበታል፡፡ በ172 ገፆች የተቀነበበው መፅሃፉ፤ በ18 ምዕራፎች የተከፋፈለ ሲሆን በ39 ብር ከ45 እየተሸጠ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡

በዘመድኩን አበራ ተደርሶ የታተመው “የምስጢሩ ጦስ” የተሰኘ ረዥም ልብወለድ መፅሃፍ ሰሞኑን ለገበያ ቀረበ፡፡
183 ገፆች ያሉት መፅሃፉ፤ “ቅድመ ታሪክ” በሚል ጀምሮ “ድህረ ታሪክ” በሚል የሚጠናቀቅ ሲሆን ዋጋው 46 ብር ነው፡፡ “የቺቺኒያ ምስጢራዊ ሌሊቶች” የሚል ሥራ ያስነበበው ደራሲው “ግዮናዊት” የሚል ቀጣይ ስራ እንዳለው በመፅሃፉ ላይ ጠቁሟል፡፡

በኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበርና በብርሐንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት በጋራ አስተዳደር ተዟዟሪ ሂሳብ ለህትመት የበቃው ‹‹ፍቅርና ተስፋ›› የተሰኘው የተሾመ ወልደሥላሴ ረጅም ልቦለድ፣ ሰሞኑን ለገበያ ቀረበ፡፡ ልቦለዱ፣ ከ1960ዎቹ ጀምሮ የነበረውን የሀገሪቱን ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ባህላዊና ሥነልቦናዊ ጣጣዎችን በመተረክ፣ ለገነገኑ ሀገራዊ ችግሮች መፍትሔ የሚጠቁም አስተሳሰቦች የተንጸባረቁበት እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡ መጽሐፉ፣ 380 ገጾች ያሉት ሲሆን፣ ዋጋው 55 ብር እንደሆነ ታውቋል፡፡
በኤርሚያስ መኮንን የተጻፈው፣ 178 ገጾች ያሉት ‹‹አጋምና ቁልቋል›› ረጅም ልቦለድም ባለፈው ሳምንት ለንባብ በቅቷል፡፡ መጽሐፉ በሽፋኑ ላይ፣ ‹‹በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተ ልብ-ወለድ›› ስለመሆኑና ‹‹ የትዳር ተጣማሪዎች በአሜሪካ የሚያጋጥማቸውን ችግርም ቁልጭ አድርጎ ያሳያል›› ሲል ጠቁሟል፡፡ በውሥጥ ገጹ ላይ ደግሞ፣ ባልተለመደ ሁኔታ ደራሲው በ1988 ዓ.ም. አድራሻው ስለጠፋበት ወንድሙ፣ ያፋልጉኝ ማስታወቂያ ያወጣ ሲሆን፣ በ39 ብር ለገበያ መቅረቡም ታውቋል፡፡

Page 7 of 16