Saturday, 21 September 2013 10:28

የአዳማ ጉዞ ማስታወሻ!

ማህደረ-ማህበራት “አንኳኩ ይከፈትላችኋል …

” “ኧረ ናዝሬት ናዝሬት፤ ረባዳው መሬት

ታበቅያለሽ አሉ፣ ሸጋ እንደ ሠንበሌጥ”

መምህር ምፅላለ-ድንግል ሙሉነህ

የዛሬው ትረካዬን እንደ መግቢያ ቁጠሩት፡፡

ሰሞኑን የተዟዟርኩት ደብረዘይት፣ አዳማ፣ እና አዋሳ ከዚያም ሻሸመኔ (አጄ) ነው፡፡ እንደተለመደው መንገድ ላይ ያጋጠመኝን ሁነት፣ ሰው፣ ተውኔትና በምናቤ የተቀረፀውን ስዕል ሁሉ ልተክርላችሁ አስቤያለሁ፡፡ በነዚህ ቦታዎች ብቻ የምወሰንም እንዳይመስላችሁ፡፡ ገና ደብረ-ብርሃን፣ ድሬዳዋ፣ ባሕር ዳር እና ዐውራምባ ድረስ እየተጓዝኩ የገጠመኝን ሁሉ፣ በራሴ ነፃነትና አካሄድ እተርካለሁ። ይህን ሁሉ እንድፈፅም ያስቻለኝን “የእየሩሳሌም ህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅትን (JECCDO) አመሰግናለሁ፡፡ (በጉዞዬ ውስጥ ይህ ድርጅት ምን አረገ፣ ከማን ጋር ምን ሠራ? ከመንግሥትና መንግሥታዊ ካልሆኑ ድርጅቶችስ ጋር ምን ምን ፈፀመ? ማለቴ አይቀርም) የጉዞዬን ማስታወሻ ለሶስት ወር በተከታታይ እተርክላችኋለሁ፡፡ መጓዝ ማወቅ ነው ብያለሁ - “የእኛ ሰው በአሜሪካን” ስፅፍ፡፡

አሁንም እላለሁ፡፡ ምናልባት የምጨምረው ነገር ቢኖር፤ መጓዝ ማወቅ ብቻ ሳይሆን ማሳወቅም ነው፤ የሚለው ነው፡፡ የናዝሬት ልጅ ነኝ - የአዳማ፡፡ እኛ ልጅ ሆነን በናዝሬት እጅግ ታዋቂ የሆነውና አንጋፋው ዕድር የአቶ ዓለሙ ወርቁ ዕድር መሆኑን ማንም ጅል አይስተውም፡፡ የዓለሙ ወርቁን ዕድር ያለዋዛ አላነሳሁትም። አንጋፋ ዕድር ነው፡፡ የአገር ጧሪ ቀባሪ ነው፡፡ የሚያውሰው ድንኳን፣ ሳህንና የብረት ኩባያው፣ አጋፋሪው፣ የዕድሩ ዳኛ፣ ሥርዓቱ፣ መቀጮው … ብዙው ነገሩ ዛሬም ውል ይለኛል፡፡ ድፍን ናዝሬት (አዳማ) አንቱ ያለው ዕድር ነው፡፡ እንደዚያ ዓይነቱ ዕድር ዛሬ ኋላ ቀር ነው ሲሉ ስሰማ ደንገጥ እላለሁ፡፡

የዛሬው የናዝሬት ጉዞዬን ልዩ የሚያደርገው፤ ያንን እኔ የማውቀውን ታላቅ ዕድር የሚበልጥ እጅግ ግዙፍ የዕድሮች ኅብረት አለ መባልን ሰምቼ የሚመለከታቸውን ሰዎች ላናግር መምጣቴ ነው፡፡ “የናዝሬት ልጅ ነኝ” አልኩት፤ ገና ስንተዋወቅ፡፡ “እኔም እዚሁ ነኝ” አለኝ፡፡ ይሄ ናዝሬት (አዳማ) ያገኘሁት ሰው ጠይም ነው፡፡ ረጅም ነው፤ መረመንጅ፡፡ የዱሮ ክቡር ዘበኛ ምልምል የመሰለ ቁመና ያለው፡፡ ዱሮ እኛ ሰቀቀሎ የምንለው ዛሬ 01 ቀበሌ የሚባለው ውስጥ ነው የተገናኘነው።

“የእንረዳዳ የዕድሮች ማኅበር” የሚባለው ቅፅር ግቢ ነው፡፡ ይሄ ሰው ከእኔ ላቅ ያለ ቁመትና ግዝፈት ይኑረው እንጂ ሲናገር ማራኪና አንደበተ - ቀና ነው፡፡ ዱሮ ደስኳሪ፣ ተናጋሪ የምንለው ዓይነት ነው፡፡ “እኔ ታምራት አስፋው ነኝ!” አለ፤ ኩራት ባለው፣ ግን ሣሣ ባለ ቅላፄ፡፡ ለስብሰባ የተዘጋጀ በሚመስል፣ ጠረጴዛና ስምንት ዘጠኝ ወንበሮች ያሉት ቦታ በጣም ተቀራርበን ተቀምጠን ነው የምናወራው፡፡ “ከአፄ ገላውዴዎስ ት/ቤት “አማርኛ አስተማሪያችንን ጋሽ ምፅላለን ታስታውሳለህ?” “ምፅላለማ አሁንም ወዳጄ ነው፡፡ ይገርምሃል ቁልጭ እንዳለ አለ!” “ዕውነትክን ነው? እኔ እሱን የማስታውስባት አንዲት የግጥም ስንኝ አለች፡- “ኧረ ናዝሬት ናዝሬት፣ ረባዳው መሬት ታበቅያለሽ አሉ፣ ሸጋ እንደሠንበሌጥ!” ተሳሳቅን፡፡ ስመ-ጥሩውን መምህራችንን በደስታ አስታወስነው፡፡

“እስቲ ስለኃላፊነትህ አውራኝ?” አልኩት፡፡ “የእንረዳዳ የዕድሮች ማህበር ሰብሳቢ ዳኛ ነኝ” ያው እኔ መቼም ከአቶ ዓለሙ ወርቁ ወዲያ ዕዳር ላሣር ነው የምል ነኝና ስለ ዱሮ ዕድሮች አነሳሁለት፡፡ “ያኛው የመሠረት ይሁን እንጂ ኋላቀር ነው፡፡ የሞተ - መቅበር፣ ማስተዛዘን፣ ድንኳን መስጠት ወዘተ ነው፡፡ “የእኛ ይለያል!” አለ ኮራ ባለ ቅላፄ፡፡ “በል እንዴት እንደምትለዩ ከዱሮው እድር (traditional) ግለጽልኝ?” አልኩት፡፡ “እዚህ ሠፈር ዕድር ውስጥ አመራር ነበርኩ። በዛን ወቅት ኤች አይ ቪ በጣም ተስፋፍቶ ነበር። ወላጅ እናት፣ ወላጅ አባት ይሞታል፡፡ ልጆች ሰብሳቢ የላቸውም፡፡ ለችግር ተጋለጡ፡፡ እነዚህ ልጆች ዕጣ ፈንታቸው ምን ሊሆን ነው? አልን፡፡ የኛስ ሚና ምን መሆን አለብን? አልን፡፡ እንደራሳችን ልጆች አየናቸውና አዘንን፡፡ ሰቀቀን፡፡ (ታምራት ዛሬ 69 ዓመቱ ነው፡፡ የልጆች አባት ነው፡፡) የወላጅ አልባዎቹን ህፃናት ነገር አነሳንና ተወያየንበት፡፡

“በጋራ እነዚህን ልጆች የማሳደግ ኃላፊነት ሊወሰድ ይገባል” አልን፡፡ ተስማማን፡፡ በዚህ መሠረት ለየዕድሩ አባላት የማስረዳት፣ የማሳመን ተግባር አስፈለገን፡፡ በነበረው በጥንቱ የእድር አደረጃጀት ሳይሆን ለየት ያለ ዓላማ የያዘ የዕድር ሂደት ነው፡፡ ዓላማችንን ግልጽ አርገን፣ ራዕያችንን ግልጽ አርገን፣ ተልዕኳችንን ግልጽ አርገን መተማመን ላይ ደረስን፡፡ እያንዳንዱ ዕድር በተናጠል የሚሠራው ሥራም መሆን የለበትም፤ አልን፡፡ አሥራ ሁለት ዕድሮችን አቀናጀን! አመራሩ አምኖበታል - አባሉም ማመን አለበት ተባባልን፡፡ መድረኮች ፈጠርን፤ እያንዳንዱ ዕድር 300፣ 400 አባላት አሉትና የማሳመን ሥራ ሠራን (awareness) ይሄ ችግር የእኛው ነው! ችግሩን ማቃለል ያለበት ሌላ አካል ሳይሆን እኛው ነን፤ አልን! ከዚያ በኋላ ከጠቅላላ ጉባዔው፣ ከህዝቡ፣ ይሁንታ አገኘን፡፡

ፕሮጄክት ዲዛይናችንን ቀረጽን፡፡ ህጋዊነት እንዲላበስ አደረግን፡፡ ከዛ ምኑ ቅጡ!...” ታምራት ሲናገር በስሜት ተጥለቅልቆ ነው። አሁን ድፍረቱ ሳይሆን ዕውነቱ ነው ፊቱ ላይ እያበራ የሚታየው፡፡ በረድ ይበል ብዬ፤ “ይሄ ማለት ከ1996 ዓ.ም ጀምሮ መሆኑ ነው?” አልኩት፡፡ “በትክክል! ከ1996 - እስከ 99ማለት ነው፡፡ ታዲያ ይህን ሥራ ስንሰራ የከተማ መስተዳድሩንም፣ የሆስፒታል አኪሞችንም፣ መድረክ ላይ እየጋበዝን እንዲናገሩ አድርገናል፡፡ የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሠራተኞችን ጋብዘናል፡፡ ሁኔታው በመንግሥትም በህዝብም ፋይዳው ምን እንደሆነ ግንዛቤ አስጨብጠናል፡፡ አየህ ብቻችንን መሥራት አንችልም

1ኛ/ ህብረተሰቡን ለማንቀሳቀስ ከመንግስት ጋር ጥሩ የሆነ የሥራ ግንኙነት መፍጠር አለብን

2ኛ/ ከግብረ ሠናይ ድርጅቶች ለምሳሌ እንደ የእየሩሣሌም የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት (ጄክዶ/Jeccdol)፣ ፎረም ኦን ስትሪት ቺልድረን፣ አክሽን የባለሙያዎች ማህበር፣ ኸልፕ ኤጅ ኢንተርናሽናል ወዘተ ዓይነቶቹ ጋር ተቀራርበን፣ ተጣጥመን መሥራት አለብን፡፡

3ኛ/ ከባለሀብቶች፣ ከዕምነት ተቋሞች ጋር ወዘተ አብረን ለመሥራት ሙሉ ግንዛቤ ወስደናል፡፡” “ከዛስ ምን አረጋችሁ? “ከዛማ በር የማንኳኳት ሥራ ነው የቀጠልነው። አንኳኩ ይከፈትላችኋል! እሹ ታገኛላችሁ!” ይላላ መጽሐፉ፡፡ በር የማንኳኳትና ዓላማችንን የማስረዳቱን ሥራ ተያያዝነው፡፡ ለየድርጅቱ፣ ለየተቋሙ፣ ለየባለሀብቱ አስረዳን፡፡ በሩ ተከፈተ! ብዙ ድጋፍ አገኘን! ሥራው እያደገ መጣ፡፡ ሥራ ክፍፍሉም በዛው መጠን ሰፋ፡፡ “መንግሥትስ እንዴት ነው? መቼም ከዕድሮች ጋር የመሥራት ፍላጐት ሳይኖረው አይቀርም?” “መጠርጠሩስ! እጅግ እጅግ ከፍተኛ ትብብር ነው ያደረገልን፡፡

አባዱላን የመሰለ ባለሥልጣን ሁለቴ ጠርተናቸው ሁለቴ ነው የመጡት፡፡ ትልቅ ድጋፍ ነው የሰጡን፡፡” “የመንግስት መሥሪያ ቤቶች በራቸው ክፍት አይደለም የሚባለውስ?” “ለእኛ? የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች በራቸው ብቻ ሳይሆን ልባቸውም ክፍት ነው፣ ነው የምንለው። ዕውነትም ክፍት ነው፡፡ እናንኳኳለን፤ እንገባለን፤ እናገኛለን! ዓላማችን ግልጽ ነው - ህፃናትንና አረጋውያንን መርዳት! እነዚህ እንዲረዱ የማይፈልግ ማነው?” አንኳኩ ይከፈትላችኋል! ነው፡፡ “አስረድተን ይሳካልናል፡፡ በተለያዩ አገራዊ ጉዳዮች ላይም አስተያየት እንድንሰጥ ይጋብዙናል። ጥሩ ግብብ አለን፡፡ ይሄን የ01 ቀበሌ ጽ/ቤትኮ እንድንሠራበት በነፃ ነው የተሰጠን፡፡” “መርሆዎቻችሁስ፣ መሪ መፈክሮቻችሁ ምን ይመስላሉ?” ግድግዳው ላይ የተለጠፉትን እይ:- “ያገሩን ሠርዶ ባገሩ በሬ!” “ድር ቢያብር አምበሳ ያሥር!” “ጋን በጠጠር ይደገፋል!” “50 ሎሚ ላንድ ሰው ሸክሙ፣ ለ50 ሰው ጌጡ!” “ዋናው ነገር ግን “አንኳኩ ይከፈትላችኋል” ነው” አለኝ በግርማ - ሞገስ፡፡ (ዝርዝሩንና ውጤቱን ሳምንት እናያለን)

Published in ባህል
Saturday, 21 September 2013 10:23

ዓለምን ያስደመሙ ተአምራት

  • የሚያማምሩ አበቦች ከሰማይ መዝነብ የወርቃማዋ ፀሐይ ተአምር
  • በደመና የማርያም መገለጥ
  • ደም የምታነባው የማርያም ስዕል

የክርስትና ሃይማኖት መሠረት የሆነው መፅሃፍ ቅዱስ በየዘመናቱ የተለያዩ ተአምራቶች መደረጋቸውን ዘግቧል። ሠዎች በተፈጥሮ ካላቸው መረዳት ውጪ የሆኑ ተአምራቶች በዚሁ ቅዱስ መፅሃፍ የተለያዩ ክፍሎች ተካተው እናገኛለን፡፡ ለምሣሌ የቅዱስ ኤልያስ ወደ ሠማይ በደመና ታጅቦ በሠረገላ ማረግ፣ የበለአም አህያ አፍ አውጥታ መናገሯ፣ አብርሃም ልጁ ይስሃቅን ለመስዋዕት ሲያቀርብ በልጁ ፋንታ እግዚአብሔር ከሠማይ በግ ማውረዱ፣ እግዚአብሔር በእጁ የፃፈው አስርቱ ትዕዛዛት ያሉበት ፅላት በቁጥቋጦ መሃል በእሣት ለሙሴ መገለፁ፣ ኤልሣዕ የተባለው ነቢይ የሞተችን ህፃን ማስነሣቱ እንዲሁም ይኸው ነብይ ባዶ የነበረን የድሃዋን ሴት የዘይት ቋት በዘይት እንዲሞላ ማድረጉ እና የመሣሠሉት ብሉይ ኪዳን ውስጥ ተጠቅሠው የምናገኛቸው ናቸው፡፡

የአይሁድ እምነትም እነዚህን ተአምራቶች ይጋራል፡፡ እነዚህን መሠል የተአምራት ዘገባዎች፣ ኢየሡስ ክርስቶስ ወደ ምድር መምጣቱንና ተልዕኮውን ፈፅሞ ወደ ሠማይ ማረጉን በሚዘረዝረው አዲስ ኪዳን መፅሃፍ ውስጥም እናገኛለን፡፡ ኢየሡስ ክርስቶስ የሞቱ ሠዎችን ማስነሣቱ፣ በጥምቀቱ ወቅትም መንፈስ ቅዱስ በእርግብ ተመስሎ በአደባባይ ከሠማይ መውረዱ፣ ኢየሡስ ክርስቶስ ሲሠቀል ምድር በቀን ጨለማ መዋጧ፣ ከዋክብት መርገፋቸው፣ የቤተ መቅደስ መጋረጃዎች መቀደዳቸው የመሣሠሉት በመፅሃፉ ክፍሎች ተአምራት ተብለው የተመዘገቡ ናቸው፡፡ በቡዲህዝም የሃይማኖት መዛግብት ውስጥም አንዳንድ ተዓምራት ሠፍረው ይገኛሉ፡፡

645-527 ዓ.ዓለም የኖረው ኢቻይዶን የተባለው የቡዲህዝም ሃይማኖት ነቢይ፤ በወቅቱ በነበረው የኮርያ ንጉስ አንገቱ ተቀልቶ እንዲሞት ሲፈረድበት፣ በሞቱ እለት ብዙ ተአምራቶች እንደሚፈፀሙ ተናግሮ ነበር፡፡ የሞት ፍርድ ሲፈፀምበትና ነፍሡ ከስጋው ሲለይ የሚከተሉት ተአምራቶች መፈፀማቸው በሃይማኖቱ ድርሣናት ተዘግቧል፡፡ በእለቱ ምድር በሃይል ተንቀጥቅጣለች፣ ፀሃይ ጨልማለች፣ የሚያማምሩ አበቦች ከሠማይ ዘንበዋል፣ አንገቱ ሲቀላ ከአንገቱ በደም ፋንታ ነጭ ወተት ፈሷል፡፡ የወተቱ ፍንጣሪም እስከ 100 ጫማ ሽቅብ ወደ ላይ ተስፈንጥሯል፡፡ ይህን ተአምር የተመለከተው የወቅቱ ንጉስ ሄይንግ ኮሡንግ ጆን፤ “ቡዲህዝም እውነተኛ ሃይማኖት ነው” ብሎ በማመኑ መንግስታዊ ሃይማኖት እንዲሆን አውጇል፡፡

በክርስትናው አለም ደግሞ ከክርስቶስ ትንሣኤ በኋላም በርካታ ተአምራቶች መፈጠራቸው ተዘግቧል፡፡ እስካሁንም ሃገራችንን ጨምሮ በተለያዩ የአለም ሃገራት የተአምራት ዘገባዎች ከአብያተ ክርስቲያናት ይቀርባሉ፡፡ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን በተለያዩ ሠዎች ታይተዋል የተባሉና እውቅና የሠጠቻቸው ተአምራት በርካታ ናቸው፡፡ ከነዚህ መካከል በ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ይኖር የነበረ እግር አልባ ስፔናዊ ወጣት፤ በፀሎት ሃይል ከጊዜያት በኋላ እግሩ እንደነበረ መመለሡ ተአምር ተብለው እውቅና ከተሰጣቸው መካከል ይጠቀሳል። ሌላው እውቅና የተሠጠው ተአምር ኦክቶበር 13 ቀን 1917 ዓ.ም በፖርቹጋል የታየው የፀሃይ ተአምር ነው።

በዚህ ተአምር ፀሃይ ለደቂቃዎች ቀለሟ ወደ ደማቅ ወርቃማነት ተቀይሯል፣ ዳንስ በሚመስል እንቅስቃሴ ውስጥ ለ10 ደቂቃ ቆይታለች፣ ወደ መሬት በጣም በመጠጋቷም ከፍተኛ ሙቀት ተከስቷል እንዲሁም በዚህ ወቅት ቀደም ብሎ በዘነበው ሃይለኛ ዝናብ የረጠበው የሠዎች ልብስ እና ምድሪቱ ክው ብለው ደርቀዋል፡፡ ይህን ትዕይንትም ከ70ሺ እስከ 10ሺ ሠዎች ተመልክተውታል ተብሎ ተዘግቧል፡፡ በዚያው በፖርቹጋል በ16ኛው መቶ ክ.ዘመን ቅድስት ድንግል ማርያም ከነልጇ በሠማይ ላይ ምስሏ በሚያንፀባርቅ ወርቃማ ቀለም ታጅቦ በደመና መሃል መታየቱ ተዘግቧል፡፡ በካቶሊክ የአስተምህሮ መፅሃፎች ውስጥ ይህን የመሣሠሉ ተአምራቶች የተመለከቱና ተአምራቶቹን ራሣቸው የፈፀሙ 41 ያህል ቅዱሣን ሠዎች ተመዝግበው ይገኛሉ፡፡

በመፅሃፍ ቅዱስ ውስጥ ያሉ ተአምራቶች በእምነቱ ተከታዮች ዘንድ በአድናቆት ተቀባይነት የማግኘታቸውን ያህል የሚቃወሟቸውም በርካታ ናቸው፡፡ ከነዚህ መካከል የአሜሪካ የአብዮት ጠንሣሽ የሚባለው ቶማስ ፔይን በብሉይ ኪዳንና በአዲስ ኪዳን መፅሃፍቶች ውስጥ የምናገኛቸው ተአምራቶች በሙሉ ሠዎች እንዲያምኑ ተቀነባብረው የቀረቡና የሚያቄሉ ናቸው ሲል በአንድ ወቅት ፅፏል፡፡ አሜሪካዊው ቶማስ ጀፈርሠን በአዲስ ኪዳን የመፅሃፍ ቅዱስ ክፍል ውስጥ ተፅፈው የሚገኙና በእሡ አመለካከት ከተፈጥሮ በላይ (Super natural) የሆኑ ተአምራቶችን የሚተርኩትን ቆርጦ በማውጣት የተሻሻለ መፅሃፍ ቅዱስ አሣትሞ ነበር፡፡ የአሜሪካ ሁለተኛ ፕሬዚዳንት የነበሩት ጆን አዳምስ በበኩላቸው፤ “እግዚአብሔር አለምን የሚገዛው በራሱ ህግ ነው ወይስ በነገስታትና በቀሣውስት ልቦለዳዊ የተአምር ፈጠራ?” ሲሉ ጥያቄ አዘል ፅሁፍ አስነብበው ነበር፡፡ ርዕሠ ጉዳዩም ለዘመናት አከራካሪ ሆኖ ዘልቋል፡፡

በቅርብ ጊዜም ለሠዎች ታይተዋል ተብለው በሃይማኖቶች ዘንድ ተቀባይነት ያገኙ፣ ነገር ግን ለሣይንስ ተመራማሪዎች ዛሬም ድረስ ግራ እንዳጋቡ የዘለቁ ተአምራቶች ተመዝግበዋል፡፡ እነዚህ ተአምራቶችም በተለያዩ አለማአቀፍ ሚዲያዎች የተዘገቡ ናቸው፡፡ About.com ካሠፈራቸው የአለማችን ምርጥ 10 የሃይማኖታዊ ሚስጥሮች እና ተአምሮች መካከል የሚከተሉት ተጠቃሾች ናቸው፡፡ የድንግል ማርያም መገለጥ ለዘመናት ድንግል ማርያም በዚህ ቦታ ተገለጠች የሚሉ ተአምሮች ተነግረዋል፡፡ ነገር ግን እውቅና አግኝተው በታሪክ ከተመዘገቡት መካከል በሜክሲኮ እ.ኤ.አ በ1531፣ በፖርቹጋል በ1917፣ በፈረንሣይ በ1858፣ በፖላንድ በ1877 ድንግል ማርያም በሠማይ ላይ በደመና መገለጧ ተዘግቧል፡፡

በክሮሽያ ደግሞ የድንግል ማርያም ምስል እስከዛሬ በተደጋጋሚ በሠማይ ላይ እንደሚገለፅ ይታመናል፡፡ በግብፅ ደግሞ በ1968 የማሪያም በደመና ታጅባ በሠማይ ላይ መገለጥ በተለያዩ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ሣይቀር እንዲተላለፍ ተደርጓል፡፡ የመላዕክት መገለጥ በአያሌ ሠዎች የመላዕክቶች መገለጥ ተነግሯል። በርካታ ፅሁፎችም ይህንኑ ትንግርት አትተዋል። እስከዛሬም መላዕክቶችን በቀን አየኋቸው፣ በሌት ተገለጡልኝ የሚሉ ግለሠቦች ለሃይማኖት መሪዎቻቸው ሪፖርት እንደሚያደርጉ ይነገራል፡፡ የቅዱሣን ስዕላት ተአምር በሠው እጅ የተቀረፁ እና የተሣሉ የድንግል ማርያም እና የኢየሡስ ክርስቶስ ምስሎች ሲያለቅሡ፣ ደም ሲፈሳቸው ተመልክተናል የሚሉ እማኞች በአለም ዙሪያ በርካታ መሆናቸውን ዘገባዎች ያስረዳሉ፡፡ በእስራኤል ቤተልሄም በሚገኝ አንድ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ውስጥ ሁሌ ደም የምታነባ የማርያም ስዕል እንዳለች ተዘግቧል፡፡

በአሜሪካ ኤሊኖስ ግዛት በሚገኝ የኦርቶዶክሣውያን ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያንም የምታለቅስ የማርያም ምስል መኖሯ ከተዘገቡት መካከል ተጠቃሽ ነው፡፡ እንዲህ መሠል ክስተቶች በካናዳ፣ በአውስትራሊያ እና በሌሎች በርካታ ሃገራት በድንቃድንቅ ሃይማኖታዊ ተአምራትነት ተመዝግበው እናገኛለን፡፡ ከነዚህ ድንቃድንቅ ሃይማኖታዊ ተአምራቶች ባሻገር የኢየሡስ ክርስቶስ ምስል በሠማይ ላይ መገለጥ በብራዚል፣ እንዲሁም የኢየሡስ ክርስቶስ መግነዘ ጨርቅ መገለጥ በጣሊያን መታየታቸውን የተለያዩ ዘገባዎች ያወሳሉ፡፡ ከክዋክብትና ከጨረቃ ጋር በተገናኘም ሃይማኖታዊ ትዕንግርት ናቸው ተብለው የሚታመኑ ተአምራቶች ተፈፅመዋል፡፡ የጨረቃ ደም መምሠል፣ የክዋክብት መርገፍ የመሣሠሉት በየጊዜው ይነገራሉ፡፡ በሃገራችንም መሠል ተአምራቶች ተከስተዋል የሚለው እንግዳ ነገር አይደለም፡፡ በደንብ የተደራጀ መረጃ ባናገኝም በብዙ የገድልና የተአምራት ድርሣናት ውስጥ የተፃፉ የተአምር መገለጥ ዘገባዎች አሉ፡፡

ምናልባትም ወደፊት ከነዚህ ተአምራቶች አንዱ ሆኖ ሊመዘገብ እንደሚችል የሚገመተው ከሠሞኑ “ከሰማይ መስቀል ወረደ” የሚለው ጉዳይም አነጋጋሪነቱ እንደቀጠለ ነው፡፡ አንዳንዶች ስለ ትዕንግርቱ ብዙ መመራመር ሳይፈቅዱ ከሠማይ መውረዱን አምነው የተቀበሉ ሲሆን አንዳንዶች ደግሞ “እንዴት ይህ ሊሆን ቻለ” በማለት እየጠየቁ ይገኛሉ፡፡ የተለያዩ ተመራማሪዎች መሠል ክስተቶችን ለበርካታ ጊዜያት በአንክሮ ያጤኗቸው ሲሆን አንዳንዶቹን ከአስማታዊ ምትሃት ጋር ሲያገናኟቸው የከዋክብት መርገፍ የመሣሠሉትን ከዩፎዎች ትዕንግርታዊ ስራ ጋር ያያይዟቸዋል። ጥቂት የማይባሉት ደግሞ እስካሁንም ምላሽ አልተገኘላቸውም፡፡ ሌሎች ትዕንግርቶች ከሃይማኖታዊ ተአምራቶች ሌላ ከተፈጥሮ ሂደት ውጪ የሆኑ ትዕንግርቶች በተለያዩ ድርሣናት ተመዝግበውና እውቅና ተሠጥቷቸው ይገኛሉ፡፡ ከነዚህ መካከል የእንቁራሪቶች፣ የአሣዎች፣ እባቦች እንዲሁም የአዕዋፋት ከሠማይ መዝነብ ተጠቃሽ ነው፡፡

ለምሳሌ ያህል በ1680 እ.ኤ.አ በሲንጋፖር እባቦች ከሠማይ መዝነባቸው ተዘግቧል። በፌብሩዋሪ 22 ቀን 1861 ዓ.ም በዚያችው በሲንጋፖር የአሣ ዝናብ መዝነቡ የተመዘገበ ሲሆን ሜይ 15 ቀን 1900 በሮድ ደሤት፣ ኦክቶበር 23 ቀን1947 በሉዚኒያ፣ ፌብሩዋሪ 12 ቀን 2008 በህንድ፣ ኦክቶበር 24 ቀን 2009 በድጋሚ በህንድ፣ ፌብሩዋሪ 25 እና 26 ቀን 2010 በአውስትራሊያ፣ ጃንዋሪ 13 ቀን 2012 በፊሊፒንስ አሣዎች ከሠማይ መዝነባቸው ተመልክቷል፡፡ የእንቁራሪቶች ከሠማይ መዝነብ ደግሞ በጁን 2009 በጃፓን፣ ከጁን 18-20 2010 ደግሞ በሃንጋሪ ተመዝግቧል፡፡ ሌሎች እስከዛሬ ምንነታቸው ያልታወቀ እንስሳትም በካሊፎርኒያ በኦገስት 1 ቀን 1869 እንዲሁም በኬንታኪ በ1876 መዝነባቸው ተመልክቷል፡፡

በ1894 ደግሞ በእንግሊዝ የጄሊፊሽ ዝናብ ተከስቷል ይባላል፡፡ በአርጀንቲናም ኤፕሪል 6 ቀን 2007 ዓ.ም ጊንጦች ከሠማይ ዘንበዋል፡፡ ተመሳሳይ ትዕንግርት በብራዚል ፌብሩዋሪ 3 ቀን 2013 ዓ.ም እንደተከሰተ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ አንዳንድ ሣይንቲስቶች የተለያዩ እንስሣትን ከሠማይ መዝነብ አስመልክተው ባሠፈሯቸው የምርምር ውጤቶች፤ ጉዳዩን ከሃይለኛ ንፋስ ጋር ያያይዙታል፡፡ በተለይ ቶርኔዶ የተሠኘው ሃይለኛ ነፋስ ሲነፍስ እነዚህ የውሃ ውስጥ እንስሣት እና ሌሎች የምድር ላይ እንስሣትን ወደ ሠማይ በማንሣፈፍ አርቆ እንደሚጥላቸው ይገልፃሉ። ቶርኔዶ የተሠኘው የንፋስ አይነት ከሃይለኝነቱ የተነሣ በሠከንዶች ውስጥ መጠነኛ የውሃ ይዘት ያለውን ሃይቅ ውሃ ጠራርጐ የመውሠድ አቅምም እንዳለው ተመራማሪዎች ያመለክታሉ፡፡

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ርዕሰ ብሔር በመሆን በሁለት ዙር ለ12 ዓመታት ያገለገሉት ፕሬዚዳንት ግርማ ወልደጊዮርጊስ፤ የስልጣን ዘመናቸው ሊያበቃ የቀራቸው ጥቂት ቀናት ብቻ ነው። ይሄም ሆኖ ግን ቀጣዩ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ማን ሊሆን እንደሚችል አሁንም ድረስ ፍንጭ አልተገኘም። የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ በፕሬዚዳንት ግርማ ወልደጊዮርጊስ የስልጣን ዘመን የስራ ክንውኖች ዙሪያ የተለያዩ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎችን ባለስልጣናትንና ምሁራንን አስተያየቶች አሰባስባለች፡፡ የ90 ዓመቱ የዕድሜ ባለፀጋ ፕሬዚዳንት ግርማ ምን ተሳካላቸው፣ ምንስ ከሸፈባቸው? እሳቸውን የሚተካው አዲሱ ፕሬዚዳንትስ ማን ይሆን? አስተያየቶቹ እንደሚከተለው ቀርበዋል፡፡

=============

“የመምረጥ እድል ቢሰጠኝ ወ/ሮ ሙሉ ሰለሞንን እመርጣለሁ” ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማሪያም ፕሬዚዳንት ግርማ እስካሁን በስልጣን ላይ ሲቆዩ ይህን ሰሩ፣ ይህን አደረጉ የምለው አንድም ወደ አዕምሮዬ የሚመጣ ነገር የለም። አንድም ጊዜ አቋም ወስደው በአገር ፖሊሲ ላይ ጫና ሲፈጥሩ አይቼም ሰምቼም አላውቅም። እንደውም እውነቱን ለመናገር ከነመኖራቸውም ትዝ አይሉኝም፡፡ አንድ ጊዜ እንደውም “አሰብ የኤርትራ አንጡራ ሀብትና ግዛት ናት” ሲሉ በጆሮዬ ሰምቼ እጅግ አዝኜባቸዋለሁ፡፡ ይህን በቴሌቪዥን ነው የተናገሩት፡፡ ቦታው ለምልክትነት ካልሆነ ብዙ የሚሰራበት አይደለም በሚለውም አልስማማም፡፡ ፕሬዚዳንቱ ሊያከናውኗቸው የሚችሏቸው የተለያዩ ተግባራት አሉ፡፡ በግልፅ የተቀመጡትን እንግዳ መቀበል፣ ፓርላማ መክፈት እና የመሳሰሉትን ትተን፣ በርካታ ስራዎችን መከወን ይችሉ ነበር፡፡ ለምሳሌ አንዳንድ የበጐ አድራጐት ስራዎችን መምራት፣ የተለያዩ ማህበራትን ማጠናከር፣ ህዝቡን ለስራ ማደፋፈር፣እስረኞችንና ህሙማንንን መጐብኘትና ያሉበትን ሁኔታ መከታተልና የመሳሰሉትን ሊሰሩ ይችሉ ነበር፡፡

ከዚህም ባለፈ የውጭ ግንኙነት ላይ የዲፕሎማሲ ስራዎች ሞልተዋል፡፡ ነገር ግን እኔ አንዱም ላይ ሲንቀሳቀሱ አላየሁም፡፡ ስለዚህ በዚህች አገር ፕሬዚዳንትነት ላይ ብዙም የሚታወሱ አይደሉም ማለት እችላለሁ፡፡ የተለያዩ የአለምና የአፍሪካ ፕሬዚዳንቶች በርካታ ስራዎችን ይሰራሉ፣ የኢትዮጵያ ፕሬዚዳንት ግን እንቅስቃሴያቸው በጣም ደካማ ነው፡፡ በቀጣይ ማን ፕሬዚዳንት ይሁን በሚለው ላይ የመምረጥ እድል ቢሰጠኝ አንድ ዕጩ አለኝ በውስጤ፡፡ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ም/ቤት ፕሬዚዳንት ወ/ሮ ሙሉ ሰለሞን ፕሬዚዳንት ሆነው ቢመረጡ በጣም ደስ ይለኛል፡፡ ይህ በተለይ ለኢትዮጵያ ሴቶች ትልቅ አቅም ይፈጥራል። አሁን ባሉበትም ብዙ እየሰሩ ነው፣ ወደፊትም ብዙ ለመስራት አቅም እንዳላቸው ይሰማኛል፡፡ በመሆኑም እጩ ምረጥ ብባል ለወ/ሮ ሙሉ ሰላምን ቅድሚያ እሰጣለሁ፡፡ “ፕሬዚዳንቱ ለሁለተኛ ጊዜ መመረጣቸው ፈፅሞ ስህተት ነበር” አቶ ሙሼ ሰሙ (የኢዴፓ ሊቀመንበር) እኔ እስካሁን በኖሩበት የፕሬዚዳንት ዘመናቸው አንድም የማስታውሰው ስኬት የላቸውም፡፡

ይህን የምልበት ምክንያት አንደኛ፣ ጤነኛ ሆነው አመቱን ሙሉ የሰሩበትን ጊዜ አላስታውስም፡፡ ሁለተኛ፣ የሰውነት አቋማቸው በንቃት እንዲንቀሳቀሱ የሚያደርጋቸው አልነበረም፡፡ በሶስተኛ ደረጃ፣ ባሉበትም ሁኔታ ይህን ሰሩ ብዬ በግልፅ የምጠቅሰው ነገር የለኝም፡፡ በዚህች አገር ጉዳይ ላይ፣ ይህችን አገር ወደፊት ያራመደ ጠንካራም ሆነ ደካማ የማስታውሰውም የማውቀውም ነገር የለም። እኔ ፕሬዚዳንት ግርማን የማውቃቸው በአገር ምልክትነታቸውና መገለጫነታቸው ብቻ ነው፡፡ ፕሬዚዳንቱ ህገ-መንግስቱ ሰፍሮ ከሰጣቸው ስልጣን ባለፈ በፕሬዚዳንትነታቸው ሊሰሯቸው የሚችሏቸው ሥራዎች ሞልተዋል፡፡ ለምሳሌ የፕሬዚዳንቱ ቦታ የዲፕሎማቲክ ስራዎችን እንዲሰሩ ያደርጋቸዋል፡፡ ብዙ ማህበራዊ እንቅስቃሴዎችም አሉ፡፡ ምናልባት አንድ ወቅት ላይ በእርሳቸው ተጀምሮ የከሸፈ ወይም የት እንደደረሰ የማላውቀው የአገሪቷ የደንና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ነበር።

አሁን በምን ሁኔታ ላይ እንዳለ አላውቅም፡፡ ነገር ግን ኢትዮጵያ ውስጥ በርካታ ሊሰራባቸው የሚገቡ ነገሮች አሉ፡፡ ለምሳሌ ከጤና፣ ከአረጋዊያን፣ ከህፃናትና ከሴቶች፣ ከህፃናት ጥቃትና መሰል ጉዳዮች ጋር የተገናኙ ሥራዎች ሞልተዋል፡፡ በፖለቲካውም ማህበራትን በማቋቋምና በማጠናከር፣ እንዲሁም በት/ቤቶች ዙሪያ ሊሰሩ የሚችሉ እጅግ በርካታ ነገሮች አሉ፡፡ ይህቺ አገር የሚያስፈልጓት ስራዎች ማለቴ ነው፡፡ እናም እርሳቸው የሀገሪቱ ምልክት እንደመሆናቸው ከተለያዩ አገራት መንግስታት ጋር እየተገናኙ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ ፋውንዴሽኖችን ማቋቋምና ማጠናከር ይችሉ ነበር፡፡ የሌሎች አገሮች ፕሬዚዳንቶች ይህንን ያደርጋሉ። በሴቶችና በህፃናት ጥቃት ጉዳይ፣ በህፃናት የትምህርት ጉዳይ፣ በጤናና በበርካታ ሚሊዮን ጉዳዮች ዙሪያ ሊንቀሳቀሱና ሊሰሩ ይችሉ ነበር፡፡ ይህቺ አገር ያለባት ማህበራዊ ችግር ሠፊና ጥልቅ መሆኑ የሚታወቅ ነው፡፡

ይህ ከማህበራዊ ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ጋር በተያያዘ ነው፡፡ በፖለቲካው ረገድ ብትወስጂው እዚህ አገር እጅግ በርካታ ችግሮች አሉ፡፡ ለምሳሌ በፖለቲካ፣ በወንጀል እና በተያያዥ ጉዳዮች ወህኒ ቤት የሚገኙ እስረኞች አሉ፡፡ የእነዚህ እስረኞች ጉዳይ መፍትሄ አግኝቶ በቀላሉ የሚፈቱበትን ሁኔታ ለማመቻቸት በሠፊው መስራት ነበረባቸው፡፡ አንዳንዱ ሰው እኮ እስር ቤት የቆየበትን ምክንያት እንኳን አያውቀውም፡፡ ከ1983 ዓ.ም ጀምሮ ከኦነግ ጋር፣ ከኦብነግ ጋርና ከተለያዩ የፖለቲካ እንቅስቃሴዎች ጋር በተያያዘ እስር ቤት ገብተው እስካሁን ያልተፈቱ ሰዎች አሉ፡፡ ይህ ጉዳይ አንድ ማህበራዊ ተቋም ተመስርቶ፣ ተጣርቶና መፍትሄ አግኝቶ መስተካከል ነበረበት፡፡ ይህን መስራት ያልቻሉት በጤናና በአቅም ሁኔታ ይመስለኛል፡፡ ከዚህ በፊት በነበረው መንግስት በርካታ ተጠቃሽ ስራዎችን ሰርተዋል፡፡ ቀላል የማይባሉ ተቋማትን በማጠናከር ረገድም ብዙ ስራዎችን አከናውነዋል፡፡ ሰውየው የብቃት ችግር አለባቸው ብዬ አላምንም፡፡ አሁን ግን የእድሜ፣ የጤናና የሰውነት አቋም ችግሮች ተደማምረው በፕሬዚዳንትነታቸው መስራት የሚገባቸውን እንዳይሰሩ አድርጓቸዋል፡፡ ይህ መቼም ግልፅና ብዙም የማያወዛግብ ጉዳይ ነው፡፡

በተለይ ሁለተኛው ተርማቸው ፈፅሞ መደረግ ያልነበረበት ነው። አሁን ኢትዮጵያ ወደፊት ለመራመድ ከምትፈልገው አቅጣጫ አኳያ ጠቃሚ ያልሆነ ውሳኔ ነበር፡፡ ኢትዮጵያ አሁን ልማት፣ እድገትና ብልፅግና ማምጣት የምትፈልግ አገር ነች፡፡ የዚያ መገለጫ የሚሆን ፕሬዚዳንት ነው የሚያስፈልጋት፡፡ ለእኔ ያንን መገለጫ የሚያሳዩ ፕሬዚዳንት አልነበሩም፡፡ እንዳልኩሽ ኢትዮጵያ ራዕይ አላት፡፡ ራዕይ ስልሽ የኢህአዴግ ራዕይ አይደለም፣ የዜጐች ራዕይ ማለቴ ነው፡፡ ያ ራዕይ ደግሞ ዜጐች ከድህነት ወጥተው፣ የተረጋጋ የኢኮኖሚና በተረጋጋ አገር ውስጥ የመኖር ራዕይ አላቸው፡፡ ይህንን ለማምጣት ደግሞ አቅምና ብቃት ያለው ገለልተኛ ፕሬዚዳንት ያስፈልጋል፡፡ ገለልተኛ ሲሆን የፖለቲካ ተቃርኖዎችን በማስታረቅና መፍትሄ በመስጠት እንዲሁም አቅጣጫ በማሳየት፣ እነዚህን ሁሉ ስራዎች ወደ ውጤት መቀየር የሚችል መሪ ይሆናል፡፡ ከላይ የተጠቀሱትን የዜጐች ራዕይ ማን ያሳካል ለሚለው፣ እከሌ ማለት ምኞት ብቻ ነው የሚሆነው። አንደኛ፣ ኢህአዴግ ይህን እድል ለማንም አይሰጥም። ሁለተኛ የራሱን ሰው መርጧል፡፡ ሲመርጥ ደግሞ በራሱ መስፈርት ነው፡፡ ከብሄር፣ ከሀይማኖትና ከመሰል ጉዳዮች አኳያ እንደሚመርጥ ነው የሚገመተው፡፡ ከዚህ በፊት በውስጤ ያሉ ሰዎች ነበሩ፡፡ አሁን ግን ከኢህአዴግ አኳያ አቅጣጫውን ሳየው፣ እከሌ ወይም እንትና ማለት ጥቅም የለውም፡፡

ስለዚህ አስፈላጊ አይደለም። ምክንያቱም ኢህአዴግ እንዲህ አይነት እድል የሚሰጥ ባህሪ የለውም፡፡ የሰዎችን ባህሪና ስነ-ልቦና አዳምጦ፣ ጠቃሚ የሆነን ሰው ወደዚያ ቦታ ለማምጣት ተነሳሽነት ያለው ድርጅት አይደለም፡፡ ስለዚህ አሁን አስተያየት መስጠት ዝም ብሎ ምኞት ብቻ ነው የሚሆነው፡፡ እኔ ደግሞ የምኞት ሰው ሳልሆን የተግባር ሰው ነኝ፡፡ “እንኳን አቶ ግርማ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳስ ምን ሰራና ነው” ፕ/ር መስፍን ወ/ማሪያም ለመሆኑ አቶ ግርማ ምን ሰርቶ ነው ስኬት ነበረው ውድቀት ነበረው የምትይው? አሁን ይሄን ጥያቄ ብለሽ ነው የምትጠይቂው ወይስ ጠፍቶሽ ነው? በመጀመሪያ ደረጃ ምን ሀላፊነት ተሰጠውና ነው ስኬት ውድቀት የምትለኪበት? የፕሬዚዳንቱ ስራ ዝም ብሎ ቁጭ ማለት ነው፡፡ ወደ 12 ዓመት ገደማ ቁጭ ብሏል ይወጣል፣ በቃ አለቀ፡፡ የምን ስኬት ነው? ምንስ ስራ ተብሎ ነው ስኬቱ የሚለካው? በመሰረቱ ህጉ ራሱ ምንም ሀላፊነት እና ሥራ አይሰጠውም፡፡ በህጉ ላይ የተወሰኑ ነገሮች አሉ፡፡ ሰዎችን መቀበል፣ እንግዶችን ማስተናገድ፣ አምባሳደሮችን መቀበልና መሸኘት፣ ይቅርታ መስጠት፣ “ይሙት በቃ” የተፈረደባቸውን ሰዎች ፈርሞ ማፅደቅ የመሳሰሉትን ያከናውናል፡፡ ይህንንም ቢሆን የሚፈፅመው ግን ከላይ ያሉት ሲፈቅዱለት ነው፡፡ ይህን ጉዳይ እናንተ ጋዜጠኞቹም ታውቁታላችሁ፣ ዝም ብላችሁ ነው የምታደርቁን፡፡

እኔ የምለው--- ከእርሱ በፊት የነበረው ፕሬዚዳንት ነጋሶ ጊዳዳስ ምን ሰራ? እንኳን አቶ ግርማ? ዝም ብሎ ተቀምጦ ኖሮ ጊዜው ሲደርስ ወጣ፣ በቃ ይሄው ነው፡፡ አንድ ሰው ስኬቱና ውድቀቱ የሚለካው ይህን ይህን ይሰራል ተብሎ በጉልህ የተቀመጠ እና ሊያሰራ የሚችል ሁኔታ ላይ ሲሆን ነው፡፡ ይሄ በሌለበት ስኬት ውድቀት የሚባለው ነገር አይገባኝም፡፡ አዲሱ ፕሬዚዳንት ማን ይሁን? ምን ይስራ? ለሚባለው የማውቀው ነገር የለኝም፡፡ እኔን ተይኝማ ጐሽ! “ፕሬዚዳንት የሚሆኑ ሰዎች ጤናማና ቀልጣፋ ቢሆኑ እመርጣለሁ” ኢ/ር ይልቃል ጌትነት (የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር) ፕሬዚዳንቱ ስኬታቸው ውድቀታቸው ምንድነው የሚለው ጥያቄ ከባድና የሚገርም ጥያቄ ነው፡፡ እኔ እንደውም ባልናገር ይሻለኛል፡፡ እንዴ! እርሳቸው ቤተ-መንግስት ገብተው ሲጦሩና ሲታከሙ ኖሩ እንጂ ምን የሰሩት ስራ አለና ነው እንደ ጥያቄ የሚነሳውስ፡፡ እናንተም ቢሆን እንዴት አንድ ነገር ሳንፅፍ ይሰናበታሉ በሚል ለወጉ ነው እንጂ ያነሳችሁት ምንም አለመስራታቸውን ሳታውቁት ቀርታችሁ አይደለም፡፡ በግላቸው በተፈጥሮ ሳይንሱና በአካባቢ ጥበቃ ላይ ፍላጐት እንዳላቸው በተደጋጋሚ ሲናገሩ እሰማለሁ፡፡ ነገር ግን ያ ጉዳይ ወደ ተግባር ተለውጦ ማየት ነበረብን፡፡

እኔ በበኩሌ ይሄ ነው የሚባል ነገር አላየሁም፡፡ እርሳቸው ርዕሰ መንግስት ሳይሆኑ ርዕሰ ብሄር ናቸው፣ ስለዚህ እሳቸው ሊሰሩ ይገባ የነበረው ይቅርታን የመስበክ፣ ሁሉንም ፓርቲዎች እኩል የማየት፣ በሀይማኖት ጉዳይ ችግር ሲከሰት የራሳቸውን አስተዋፅኦ ማድረግ ነበር፡፡ ነገር ግን እርሳቸው ጤናቸውም፣ እድሜያቸውም ምክንያት ሆኖ የስራ እንቅስቃሴያቸው ትክክለኛ ፕሬዚዳንት ሊያደርገው የሚችለው አይነት አልነበረም፡፡ በሁለተኛ ደረጃ፣ እርሳቸው ኢህአዴግን ከማመን ውጭ በራሳቸው ተንቀሳቅሰው ይህን አደረጉ የሚባልላቸው ነገር የለም፡፡ በሶስተኛ ደረጃ፣ ቦታውም ሆን ተብሎ በህገ-መንግስቱ ሲፀድቅ ባዶ ከመሆን የማይሻል ተደርጐ ስለሆነ እኔ እንደ አንድ የፖለቲካ ቁምነገር ለማየት እቸገራለሁ፡፡ በነገራችን ላይ ህገ-መንግስቱ ላይ ባይቀመጥም ፕሬዚዳንቱ ብዙ ሊሰሯቸው የሚገቡ ነገሮች አሉ፡፡ እርሳቸው ግን ምንም አላደረጉም፡፡ ለምሳሌ በሀይማኖቶች አካባቢ ያለውን እንመልከት፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ለሁለት ተከፍሎ ችግር ላይ ነበር፡፡ በአንድ ወቅት እነዛም ከውጭ ይምጡና ይወዳደሩ የሚል ሀሳብ ካቀረቡ በኋላ፣ ፖለቲከኞቹ ሲቆጧቸው ሀሳቡን አንስቻለሁ አሉ። በእስልምና እምነት ተከታዮች መካከል ይህ ሁሉ ችግር ሲፈጠር፣ እንደ ርዕሰ-ብሄርነታቸው መንግስት ከዚህ ጨዋታ እንዲወጣና ችግሮቹ መልክ እንዲይዙ ማድረግ ይችሉ ነበር፡፡ በምርጫው ጊዜ በፓርቲዎች መካከል አለመግባባት ሲፈጠር ወደ እርቅ፣ ወደ መቻቻልና ወደ ሰላም እንዲመጡ የራሳቸውን አስተያየትና ሀሳብ መስጠት ይችላሉ፡፡

እንደርዕሰ ብሄርነታቸው ጐላ ባለ መልኩ ሊሰሯቸው የሚችሏቸው በርካታ ነገሮች ነበሩ፣ ነገር ግን እንደነገርኩሽ ዕድሜያቸውም ሆነ ጤናቸው እንዲሁም አጠቃላይ ሁኔታቸው ያንን እንዲከውኑ አላደረጋቸውም። በዘመኑ ቋንቋ “ከደረጃ በታች ተጫውተዋል” ነው የእኔ አስተያየት፡፡ በትምህርት ዝግጅት፣ በዲፕሎማሲ በአጠቃላይ ሁኔታዎች እከሌ ቢመረጥ የምትለው አለ ወይ ለተባልኩት እኔ በእውነቱ ምንም እከሌ የምለው ሰው የለኝም፡፡ አንደኛ የሚመረጠው ሰው በኢህአዴግ ኮረጆ ውስጥ ገብቶ ነው የሚሰራው፡፡ ሁለተኛ ቦታውም እዚህ ግባ የሚባል ስልጣን በህገ-መንግስቱ አልተሰጠውም፡፡ የሚወዳደሩትም ሰዎች በብዛት እዚያ ሲስተም ውስጥ የሚገቡት በዚህ ታሪክ ውስጥ ስማችን ተመዝግቦ እናልፋለን ብለው እንጂ ቦታውን አሁን ባለው ሁኔታ ቁም ነገር እንሰራበታለን ብለው አይደለም፡፡ ስለዚህ ለእኔ ማንም ተመረጠ ማን ለውጥ አያመጣም፡፡ ነገር ግን ጨቋኞች ቢሆኑም የአገር ምልክት ናቸውና ጤነኛ፣ የተማረ፣ ተነጋግሮ በቋንቋ የሚግባባ ሰው፣ በተቀላጠፈ ሁኔታ የሚንቀሳቀስና ያሉትንም ውስን ስራዎች የሚያከናውን ቢሆንና አገር ባይዋረድ እመርጣለሁ፡፡

ከዚህ ባለፈ በስራ ደረጃ ፕሬዚዳንቱ ይህን ሰርቶ፣ ይህን አድርጐ ለውጥ ያመጣል በሚል የምጠብቀው ምንም ነገር የለም፡፡ “ፕሬዚዳንት በህገ-መንግስቱ የተቀመጠላቸውን ሀላፊነት በአግባቡ ተወጥተዋል” ዶ/ር አሸብር ወ/ጊዮርጊስ ፕሬዚዳንቱ ይህን ሰሩ ወይም አልሰሩም ለማለትም በህገ-መንግስቱ የተቀመጠላቸውን አቅጣጫ ማየት ግድ ይላል፡፡ በህገ-መንግስቱ የተቀመጠና የተሰጣቸው የስራ ሀላፊነት አለ፣ ያንን ከመወጣት አኳያ በተገቢው መንገድ ተወጥተዋል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ከዚህ ውጭ በግላቸውም በተለይ አካባቢንና ተፈጥሮን ከመንከባከብ አኳያ የጀመሩት ስራ በጥሩ ሁኔታ ተከናውኗል የሚል እምነት አለኝ፡፡ የእኛ አገር አካሄድ በአብዛኛው ፓርላሜንታሪ ነው፡፡ በፓላሜንታሪ አገር ደግሞ ብዙውን ስራና ሀላፊነት የሚጥለው በጠቅላይ ሚኒስትሩ ላይ ስለሆነ ባልተሰጣቸው ሀላፊነት ስራ አልሰሩም ተብሎ የሚወቀሱበት ሁኔታ ያለ አይመስለኝም። ህገ መንግስቱ የፈቀደላቸውን ግን በአግባቡ ተወጥተዋል ባይ ነኝ፡፡ ይቅርታ በማድረግ፣ አምባሳደሮችን በመሾም እና በመሰል ጉዳዮች ላይ ሰርተዋል ወይ ከተባለ፣ አዎ ሰርተዋል። ሹመቶቹንም ቢሆን ቀጥታ መሾም ሳይሆን በጠቅላይ ሚኒስትሩ አቅራቢነት ነው የሚሾሙት፣ ስለዚህ ስራቸውን ተወጥተዋል፡፡ ስለወደፊቱ ፕሬዚዳንት አመራረጥ መነሻው ህገ-መንግስቱ ነው፡፡

በህገ መንግስቱ መሰረት ለገዢው ፓርቲ የተሰጠ ስልጣን አለ፡፡ ገዢው ፓርቲ ነው ፕሬዚዳንቱን የሚያቀርበው፣ ስለዚህ ስለ ቀጣዩ ፕሬዚዳንት ከዚህ በላይ ማለት አልችልም፡፡ “ፕሬዚዳንት ግርማ ስኬታማም እድለኛም መሪ ናቸው” “የቀጣዩን ፕሬዚዳንት ማንነት መተንበይ አልችልም” አቶ አሰፋ ከሲቶ የፕሬዚዳንቱ አማካሪ የፕሬዚዳንት ግርማ ዋናው ስኬት ለሁለት ጊዜ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በዴሞክራሲያዊ መንገድ የመረጣቸው መሆኑ ነው፡፡ ከዴሞክራሲ ሂደቱ አንፃር ይሄ ትልቅ ስኬት ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ በራሳቸው ለህዝብ አርአያ የሚሆን በርካታ ስራዎችን ላለፉት 12 ዓመታት ሲያከናውኑ ነው የቆዩት፡፡ የህዝብ አገልጋይነትን ስሜት ይዘው ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ህዝብ ማገልገል መቻላቸው በጣም አስደሳች ነው፡፡ ለምሳሌ የተቸገረ ሰው ወደ እርሳው አቤቱታ ባቀረበ ጊዜ ችግሩ እንዲፈታ ያደርጋሉ፡፡ የቅርብ አማካሪ እንደመሆኔ የእርሳቸውን ውሳኔና ድጋፍ ሊያገኝ የመጣ ሰው የእርሳቸውን ድጋፍና ምክር አግኝቶ የሚሄድበት ሁኔታ እንደነበር አውቃለሁ በአጠቃላይ ዜጐችን የማገልገል እምነታቸውና ፍላጐታቸው ጠንካራ መሆኑን ለማስተዋል ችያለሁ፡፡ በሌላ በኩል እውቀታቸው ከምንምና ከማንም ጋር ተወዳዳሪነት የሌለው ነው።

ለምሳሌ የቋንቋ ችሎታቸው በጣም ሰፊ በመሆኑ ከማንኛውም አገር መሪና ኤምባሲዎች ጋር በመገናኘት በፈለጉት ቋንቋ ሀሳባቸውን የመግለፅ ብቃታቸው ወደር የለውም፡፡ እንግሊዝኛ፣ ፈረንሳኛ፣ ጣሊያንኛና ሌሎችንም ቋንቋዎች አቀላጥፈው መናገር የሚችሉ በመሆናቸው ስለ አገሪቱ ጠቅላላ ሁኔታ በእድገት ጉዞና በተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ የአገርን ገፅታ ግንባታ በመስበክ ስኬታማ መሪ ናቸው፡፡ በጣም አንባቢ ናቸው፡፡ የማስታወስ ችሎታቸው ፍፁም የሚደነቅና ወደር የለሽ ነው፡፡ በዚህ ለሌሎች አርአያ መሆን የሚችሉ ናቸው፡፡ ሌላው ማረሚያ ቤት ገብተው የታረሙ ሰዎች ይቅርታ አግኝተው እንዲወጡ ከፍተኛ ክትትል ያደርጋሉ። አንድ ሰው ወንጀል ፈፅሞ በፍ/ቤት ፍርድ ተሰጥቶ ማረሚያ ቤት የገባ ሰው መታረሙ ከተረጋገጠ ማረሚያ ቤት እንዲቆይ አይፈልጉም፡፡ ታራሚው ከማረሚያ ከወጣ በኋላ ችግር የማይፈጥር መሆኑን እንደ ይቅርታ መስፈርት ይወስዱታል፡፡ እንደውም በአንድ ወቅት የነገሩኝን ባነሳ ደስ ይለኛል፡፡ በ1950ዎቹ ኢሉባቡር ጐሬ ውስጥ ለስራ በሄዱ ጊዜ 15 ሰዎች መንገድ ላይ ቆመው ያገኛሉ። ከመኪና ወርደው “ምንድናችሁ?” ብለው ሲጠይቁ፣ እስረኞች እንደሆኑ መለሱላቸው ከመሀላቸው አንዱ ጠብመንጃ ይዟል፡፡

“አንተስ ጠብመንጃ የያዝከው ምንድነህ?” ብለው ይጠይቁታል፡፡ “ወደ መቱ አጅቦን የሚሄደው ፖሊስ ሊፀዳዳ ወደ ጫካ ገብቶ ጠብመንጃውን ያዝ ብሎኝ ነው” አላቸው፡፡ እርሳቸውም በጣም ተገርመው በወቅቱ መቱ ጠቅላይ ግዛት ሀላፊ ለነበሩት ሰው ደብዳቤ ፅፈው እንዲፈቱ አድርገው ወደ አዲስ አበባ መመለሳቸውን አጫውተውኛል፡፡ እናም የታረሙ ሰዎች እስር ቤት እንዲቆዩ አይፈልጉም፡፡ እድለኛ ናቸው የምለው ደግሞ በእርሳቸው ዘመን ታላቁ የህዳሴ ግድብ በመጀመሩ ነው፡፡ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድም ውጤታማ በሆነ መንገድ ተፈፃሚ እየሆነ ያለበት ወቅት በመሆኑም ስኬታማም እድለኛም ናቸው እላለሁ፡፡ እስካሁን እንደ ርዕሰ ብሄርነታቸው በህገ-መንግስቱ አንቀፅ 11 መሰረት የተሰጣቸውን ስልጣንና ተግባር ሙሉ ለሙሉ በአግባቡ እንደተወጡ አምናለሁ፡፡ በአስፈፃሚ አካል ስልጣንና ሃላፊነት ጣልቃ አይገቡም፡፡ ጠንካራና ታታሪ ሰራተኛ ናቸው፡፡ ለምሳ የማይወጡበትቅ ጊዜ ይበዛል፡፡ ሀላፊነታቸውንና ተግባራቸውን በአግባቡ ተወጥተዋል፡፡ እርሳቸውን ተክቶ የሚሰራውን ሰው መገመት አልችልም፡፡ በህገ መንግስቱ በተቀመጠው መሰረት ቀጣዩ ፕሬዚዳንትም በህዝብ በተወካዮች ም/ቤት እና በፌዴሬሽን ም/ቤት ስብሰባ ተደርጐ በውይይት ተመርጦ ነው የሚቀርበው፡፡ በመሆኑም የቀጣዩን ፕሬዚዳንት ማንነት መተንበይ አልችልም፡፡ የማውቀውም ነገር የለም፡፡

ኢትዮጵያዊነት ግትርነት ከሆነ፣ አዎ ግትር ነኝ ደህና ተቃዋሚን ለመፍጠር ከልብ ከሆነ ጊዜ አይፈጅም አልዘፍንም እንጂ ሰው ሲዘፍን ለማየት የትም እገባለሁ

በምርጫ 97 የቅንጅት ለአንድነትና ለዲሞክራሲ ሊቀመንበር የነሩትና ከመኢአድ ሊቀመንበርነታቸው በቅርቡ የለቀቁት ኢንጂኒየር ሃይሉ ሻውል “ህይወቴና የፖለቲካ እርምጃዬ” በሚል ርዕስ የፃፉትን ክፍል አንድ መፃሐፋቸውን ከሰሞኑ ለንባብ ማብቃታቸው ይታወሳል፡፡ የመጽሐፉ ቀጣይ ክፍል ለንባብ እንደሚበቃና ስላለፉባቸው የስራና የፖለቲካ ሃላፊነቶች በዝርዝር የሚያትት አዲስ መጽሐፍ በእንግሊዝኛ ቋንቋ እየፃፉ መሆናቸውን ከገለፁት ከኢንጂኒየር ሃይሉ ሻውል ጋር ኤልሳቤት እቁባይ ለንባብ በበቃው መጽሐፋቸው ዙሪያ ቆይታ አድርጋለች፡፡

እርስዎ ያለፉባቸውን ሶስቱን መንግስታት እንዴት ያነፃጽሯቸዋል? ሶስቱን መንግስታት ማነፃፀር ያስቸግራል። ምክንያቱም ብዙ ሰው የሚያየው ከራሱ ጥቅም አንፃር ብቻ ነው፡፡ እኔ የራሴን ጥቅም መለኪያ አድርጌ አላየውም። የማይበት መነጽር ህዝብ ምን ሁኔታ ላይ ነው የሚለውን ነው፡፡ ሶስቱም ላይ ችግር አለ፡፡ በቀዳማዊ ኃይለስላሴ ጊዜ ጥቂት ግለሰቦች ያለእኛ ሰው የለም እያሉ፣ ህዝቡን ሲያበሳጩ አይቻለሁ፤ እኔም ራሴ ደርሶብኛል፡፡ ምን ደረሰብዎት? ኩሊ ተብያለሁ፡፡ ምክንያቱም ካኪ ለብሼ ቆሜ ስለምሰራ፡፡ ሰው የሚባለው ክራባት አስሮ ቢሮ ውስጥ ሰርቶ፣ ከዛ ሲወጣ ደግሞ ኢትዮጵያ ሆቴል ሄዶ እየተንዘባረረ ሲጠጣ ነው፡፡ ለኔ ደግሞ ሰው ማለት የትም ገባ የት ውጤት ሲያመጣ ነው፡፡ እኔ መጀመሪያውኑ ከውጭ ተምሬ ስመጣ ቀጥታ ገጠር ነው የገባሁት፡፡

አዲስ አበባ ቤት አልነበረኝም፡፡ ያን ጊዜ እንደኔ አይነት ሰው ዋጋ አልነበረውም፡፡ የታወቁ ህዝብን የሚያጐሳቁሉ ሰዎች ነበሩ፡፡ ሆን ብለው ችግር የሚፈጥሩ፡፡ ችግሮችን ሁሉ በስርዓቱ ላይ ማላከክ ተገቢ አይደለም፡፡ በእርግጥ ስርአቱ ለሀብታም ያደላል፡፡ ዞር ብለው ደግሞ ለደሀ ልጅ ነፃ የትምህርት እድል ይሰጣሉ፡፡ ከዜሮ ክፍል እስከ ማስተርስ ዲግሪ ያስተምራሉ፡፡ ለደሀ እድል ተሰጠ ማለት ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ የመደብ ልዩነት የለም። ልዩነቱ ያለው በምታገኘው ገቢ፣ በምትሰሪው ስራ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በሁሉም መደቦች ለማረፍ የተመቻቸ ያደርገዋል። ካንቺ የሚጠበቀው ለምትሰሪው ስራ ትኩረት መስጠት ነው፡፡ ሠራተኛ ከሆንሽ አለቃሽንም Go to hell ማለት ትችያለሽ፡፡ እኔ እንደዚያ እል ነበር፤ ማንም የነካኝ የለም። ደርግ የአፄ ኃይለስላሴን መንግስት ሌት ተቀን እንደወቀሰ ሄደ፡፡ ኃይለስላሴ እንዲህ አድርጐ፤ መሬት ነጥቆ ይል ነበር። እነሱ ምንድን ነው ያደረጉት? የነጠቁት እኮ እነሱ ናቸው፡፡

ስንት የደሀ ልጅ ለፍቶ ያገኘውን ነጥቀው ባዶ እጁን አስቀሩት፡፡ በኢትዮጵያ ስራ ፈጣሪነት ሞተ። ኢትዮጵያን ለውጭ ዜጐች ያመቻቸውም ይሄ ነው። ምክንያቱም ድሮ ቆጣቢ የነበረው እንደ ደርግ መጥቶ የሚወስድብኝ ከሆነ፣ ለምን አስቀምጣለሁ ማለት ጀመረ። ሶስተኛው መንግስት ደግሞ በዛው ላይ ገነባበት፡፡ ከህዝብ የተወሰደውን በራሱ እጅ አደረገ፡፡ ገጠር ብትሄጂ እያንዳንዷ ኩርማን መሬት የመንግስት ናት፡፡ ገበሬው እናገራለሁ ቢል ከመሬቱ ላይ ይባረራል፡፡ ከተማ ሰማያዊ ቁምጣ ለብሶ የሚመጣው ማን ነው? ባለስልጣን ከመሬቱ ያባረረው ገበሬ ነው፡፡ በሱ ቦታ ላይ እርሻ ምን እንደሆነ የማያውቅ፣ የፖለቲካ ወሬ ህዝብ መሀል ቆሞ የሚጮህ ተተካበት፡፡ ስለዚህ ረሀብ መጣ፤ ምርታማነት አሽቆለቆለ። ዛሬ ያን ለመመለስ እያሉ በቴሌቪዥን የሚያወሩት ነገር አያስኬድም፡፡ እነሱ የሚያወሩትን የዘር ጉዳይም እኔ የትም አላገኘሁትም፡፡ ምናልባት ያለው ህወሓት የተፈለፈለበት ቦታ ሊሆን ይችላል፡፡ ትግራይንም አውቀዋለሁ። ትምህርት እንደጨረስኩ መጀመሪያ ሱፐርቫይዝ ለማድረግ የሄድኩት መቀሌ ነው፡፡ በህዝቡና በእኔ መሀል አንድም ልዩነት አልነበረም፡፡ ተከባብረን ተዋደን ነው ስንሰራ የነበርነው። በርግጥ በአማራ እና በትግሬ መካከል የስልጣን ሽሚያ ነበር፡፡ እነሱ --- በህዝብ መሀል ድንበር ሰሩ፡፡ አሁን ነገሮች እየተለወጡ ነው፡፡ የደቡብ ህዝብ ከማንኛውም ዘር ጋር ችግር የለበትም፡፡ በቅርቡ አማራ ከደቡብ ይውጣ ሲል በፅሁፍ ያዘዘው ባለሥልጣን፣ አሁን ትምህርት ሚ/ር ሆኗል፡፡

ምን እንዲያስተምረን አስበው እንደሾሙት አላውቅም፡፡ ህዝቡ ቢፈልግ ኖሮ አማራውን በሁለት ቀን ያስወጣው ነበር፡፡ ህዝቡ ግን ስላልፈለገ እግሩን እየጐተተ ሳለ ነው ካድሬዎቹ አስወጡ ተብለው የተላኩት፡፡ እኛ ህዝቡ ተጐዳ ብለን ጮኸናል፡፡ ጉዳቱ ለሚባረረው ብቻ አይደለም፡፡ ለቀሪውም ጭምር ነው፡፡ መንግስት እንዲህ ያሉትን ችግሮቹን በጊዜ ካላስተካከለ ከሁሉም የባሰ ነው የሚሆነው፡፡ በመጽሐፍዎ ላይ “ከአባይ ሸለቆ ጭቅጥቅ ስለማልፈልግ ለቀቅሁ” ብለው የፃፉት ነገር አለ፡፡ ጥቅጥቁ ምን ነበር? አባይ ሸለቆ በጣም የወደድኩት ስራ ነበር፡፡ በገደል ላይ ተንጠልጥዬ ነፍሴን ሸጬ የሰራሁበት መ/ቤት ነው፡፡ ሠራተኛው በሙሉ ጐበዝ ነበር፡፡ መንገድ በሌለበት መንገድ ቆፍረን ነበር የምናልፈው፡፡ ስለዚህ አባይ ሸለቆን መተው ማለት ትልቅ የራሴን አስተሳሰብና ሃይል ጥሎ እንደመሄድ ነው፡፡ ወጣም ወረደ ስራው ውጤታማ ሆኗል፡፡ እኛ ስራ ስንጀምር ቢሮክራሲ አልነበረም፡፡ የውጪ ዕርዳታ ነበር፡፡ ስራችንን በተፈለገው መሠረት እንሠራለን፡፡ እጅ መንሳት ምናምን ግን የለም፡፡ በኋላ አንድ ኢትዮጵያዊ ዳይሬክተር ሆኖ ተሾመ፡፡

በሙያ ደረጃ ከፍተኛ ምሁር ነበር፡፡ ነገር ግን ቢሮ አናየውም፡፡ እሱ ጋ የተጠጉትም ምንም የማይረቡ ነበሩ፡፡ የምንሰራውን መንካት ጀመሩ፡፡ ዳይሬክተሩ ስራውን ትቶ ጃንሆይ የሆነ ቦታ ይሄዳሉ ሲባል ምንጣፍ በትክክል ተነጠፈ አልተነጠፈም የሚለውን የሚያይ መሀንዲስ ሆነ፡፡ “ሰውየው ምህንድስናው የምንጣፍ ሳይሆን አይቀርም” እያልን እንሳሳቅ ነበር፡፡ ቢሮክራሲው በጣም ሲያስቸግር ለመልቀቅ ወሰንኩ፡፡ ከአንድ ወር በኋላ ወጥቻለሁ አልኳቸው፡፡ የእውነት አልመሰላቸውም፡፡ ወሩ ሲሞላ ቀረሁ፡፡ ከዛ ሼል ኩባንያ ያወጣውን ማስታወቂያ አንብቤ አመለከትኩ፡፡ ቃለመጠይቁን ከእንግሊዝ ከመጣ ሰው ጋር አደረግሁና፤ ከአንድ ወር በኋላ ስራ ጀመርኩ። ደቡብ የመን የአውሮፕላን ጣቢያ ግንባታ ሱፐርቫይዝ እንዳደርግ ተላኩ፡፡ ወር ሳይሞላኝ ወደ ኢትዮጵያ መመለስ አለበት ተባለና፣ ስመለስ የተሳፈርኩበት አውሮፕላን ውስጥ ለኢትዮጵያ ከተመደበ አዲስ የሼል ማኔጀር ጋር ተገናኝተን ስናወራ “ለምን ቶሎ ተመለስ አሉህ?” አለኝ፡፡ “እኔ አላውቅም፤ ምናልባት መንግስት ይሆናል” አልኩት፡፡ ልክ እንደደረስን ከመንግስት ፈቃድ ሳያገኝ የወጣ ስለሆነ አባሩት የሚል ደብዳቤ ተጽፎላቸዋል፡፡ እኔም ብትፈልጉ ከስራ አስወጡኝ እንጂ አልመለስም አልኩ።

አዲሱ ማኔጀር ለደብዳቤው መልስ አልሰጥም ብሎ ዘጋቸው፡፡ የበፊቱ እንግሊዛዊ ግን ከመንግስት ጋር ያጣላናል ብሎ ነበር፡፡ ሼል አስራ ሶስት አመት የሰራሁት የኔን አመል ችለው ነው፤ አንድ መ/ቤት ውስጥ ብዙ መቀመጥ አልወድም በማለት መጽሐፍዎ ላይ ገልፀዋል። ለምንድነው በአንድ መ/ቤት ብዙ መቆየት የማይወዱት?… ሼል እኮ ብዙ ቆየሁ፡፡ እነሱ በየጊዜው ደሞዝ ይጨምራሉ፡፡ ለማቆየት ብዙ ነገር ያደርጋሉ፡፡ መጨረሻ ላይ አንድ ትልቅ ብድር ሰጡኝ፡፡ ቤት ሥራ ብለው። ቀደም ብሎም አንድ ትንሽ ቤት ስሰራ አበድረውኛል። ገንዘቡ ቶሎ የማይከፈል ስለሆነ መያዥያ ነው፡፡ ምክንያቱም ብዙ ስልጠና ሰጥተውኛል፡፡ እሺ አልኩና ብድሩ ስለተጫነኝ አስራ ሶስት አመት ቆየሁ፡፡ በዛን ወቅት ኢትዮጵያ ውስጥ ችግር አልነበረም፡፡ የፈለጉበት ሄዶ መስራት ይቻላል፡፡

ኮካኮላ ካምፓኒ፣ሊባኖስ ናና ለኛ ስራ አሉኝ፡፡ አበሻ ስለሆንኩ ይሉኝታ አስቸገረኝ፡፡ ቀረሁ፡፡ በኋላ ለውጥ ሲመጣ ለቀቅሁ፡፡ ልዩ ልዩ ስራ ላይ ስለሚያሰሩኝ አይሰለቸኝም ነበር፡፡ መሀንዲስ ሆኜ ገባሁ። ከዛ የትራንስፖርት ኤክስፐርት ሆንኩ፡፡ በመቀጠል ሊቢያ ሄጄ ሠራሁ፡፡ ከዛ ሽያጭ ክፍል ገባሁ፡፡ እድገት አግኝቼ ወደ ምክትልነት ስደርስ “አንተ ውጪ አገር ተልከህ ሼል ኩባንያ መስራት አለብህ” አሉኝ፡፡ ለምን ስል፣ የኩባንያ ሃሳብ እንዲኖርህ ሲሉኝ፣ ይህን ሁሉ አመት ሰርቼ አልኳቸው፡፡ በኋላ ሳስበው በአንድ ወቅት የእንግሊዝ ፓውንድ የመግዛት አቅሙ ወርዶ አተረፈና ሪዘርቭ ሊያደርጉ ሲሉ፣ “ትርፍ ስለሆነ ዲክሌር አድርጉ” ስላልኩ የኩባንያ ታማኝነት የለውም አሉ፡፡ ከዛ እንግሊዝ አገር ሂድ ተባልኩ፡፡ በደሞዝ ለመጣላት ሞከርኩ። እንግሊዞቹ ኢትዮጵያ ሲመጡ ከደሞዛቸው ውጪ ብዙ ይከፈላቸዋል፡፡ እኔን ግን ልክ አንድ እንግሊዛዊ እንደሚከፈለው ሊከፍሉኝ ወሰኑ፡፡ አይ አልኩ፡፡

የአየር ፀባዩ አይስማማኝም፡፡ ርካሽ እቃ የሚገዛበትን አላውቅም። እናንተ እዚህ ቆንጆ የአየር ፀባይ ያለው አገር መጥታችሁ ልዩ ክፍያ ስለሚሰጣችሁ አልስማማም አልኩ፡፡ አፍሪካ ውስጥ አድርገን አናውቅም ሲሉ፤ አሁን ጀምሩ አልኳቸው፤ እሺ በሚስጥር ብለው ጀመሩ፡፡ እዚህ ሂደት ላይ ሳለን ለውጥ መጣ፡፡ እስከዛሬ የማማርረው ቢሮክራሲ አለ ብዬ ነው፡፡ አሁን ለምን ፈረንጅ አገር እንደገና እሄዳለሁ ብዬ ሳስብ፣ የስራ ሚኒስትር “አውራጐዳና ችግር ተፈጥሯል፤ አግዘን፤ ሠራተኛው በር ዘግቶ ማኔጀሮቹን፣ ኢንጀነሮቹን አባረረ አለኝ፡፡ ታድያ ምን ላድርግ ስለው፤ አግዘን አለኝ፡፡ በቋሚነት ሳይሆን በኮንትራት እሠራለሁ ብዬ ተስማምተን አውራ ጐዳና ገባሁ፡፡ ከደርግና ከተለያዩ የፖለቲካ ጐራዎች የግድያ ሙከራዎች ተርፈዋል፡፡ እስቲ ስለሱ ይንገሩኝ --- ያን ጊዜ ሁሉም ግራ ዘመም ፖለቲከኛ ነበር። እኔ ደግሞ አንዳቸውንም ማስጠጋት አልፈለግሁም፤ ምክንያቱም ጥፋት እንጂ ልማት የላቸውም፡፡

የገባሁባቸው መስሪያ ቤቶች ደግሞ ብዙ ወዛደር ያለባቸው፣ ብዙ ገንዘብ የሚዘዋወርባቸው ስለሆኑ ሁሉም በእጃቸው ማስገባት ይፈልጉ ነበር፡፡ ኢህአፓ እና ኦነግ አንዱ በወንጂ በኩል፣ ሌላው በመተሀራ ተጠናክረው እርስበርስ ሲፋጁ ነበር፡፡ እኔ ለሁለቱም እድል አልሰጠሁም፡፡ ስራ የምንሰራ ከሆነ እነዚህን ወደ ዳር ማውጣት አለብን አልኩ፡፡ ሠራተኛው አልገባውም፡፡ ደርግም መጥቶ እንደማያድነኝ አውቃለሁ፡፡ ምክንያቱም የግራ ክንፍ ፖለቲከኞች ናቸው፡፡ የመጀመሪያ ጊዜ የመውደድ፣ የመደገፍ ጉዳይ አለ፡፡ የወዛደር አምባገነንቱም አለ፡፡ የወንጂዎቹ ብዙም አስቸጋሪዎች አልነበሩም፡፡ ማታ ከማህበር መሪዎች ጋር ቁጭ ብዬ አወራለሁ፡፡ “ድርጅቱ ቢዘጋ ቤተሰባችሁ ምን ይሆናል? ችግር ሲኖር ለኔ ንገሩኝ እንጂ ድርጅቱን አትጉዱ” በሚል ተስማማን፡፡ የመተሀራዎቹ ግን አናዳምጥም አሉኝ፡፡ አንድ ቀን ስሄድ አንድ መሀንዲስ ሚኒስትር ሆኗል፡፡ ወዛደሩ ከቦ ይዞታል፡፡ ቀጥታ ገባሁና ልጁን እጁን ይዤ ወጣሁ፡፡ ከወጣሁ በኋላ ተጯጯሁ፤ ዝም አልኳቸው፡፡ በኋላ ሊገድሉኝ ሞከሩ፡፡ በሳር ቤት በኩል ነበር፡፡ አንዱ መሳሪያ ይዞ ሲሄድ አይቼዋለሁ፡፡

“ገልጃጃ ነው፤ እኔን ፍለጋ መጥቶ ከጀርባው ስሄድ የማያውቅ” ብዬ ጥዬው ሄድኩ፡፡ መተሀራ ያሉት ከቤትህ አትውጣ አሉኝ፡፡ እኔ ያኔ አልፈራም ነበር፡፡ ልጆች ከመጡ ወዲህ ነው ፍርሃት የሚባል ነገር የመጣብኝ፡፡ ስብሰባም ላይ Shut up ነው የምለው፡፡ ያኔ በዛ ባላቆም ኖሮ ተያይዘን ነበር ገደል የምንገባው፡፡ በወቅቱ ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲ “እኔ ነኝ አሸናፊ” ብሎ ደምድሟል፡፡ ደርግ ደግሞ “እስቲ ይሞክሩኝ” ይላል፡፡ በሽታው አዲስ አበባ መጣ፡፡ አንድ ሠራተኛ ለመያዝ ብለው ቤቱን ከበዋል፤ ቢሮአችን ፊሊፕስ ህንፃ ነበር፡፡ ምንድን ነው ይህ ሁሉ ሚሊሺያ ብዬ አልፌያቸው ገባሁ፡፡ ልጁን እንፈልጋለን አሉ፤ ውሸታቸውን ነው፤ ቀጥታ እኔ ቢሮ ነው የመጡት፡፡ ሁሉም መሳሪያ ደግነው መሳቢያዬን ከፈቱ፤ መሳሪያ ያለኝ መስሏቸው ሲያጡ “አንተ ሲአይኤ ነህ” አሉና ወሰዱኝ፤ አስፈራሩኝ፡፡ ከአውራ ጐዳና ያመጧቸውም ነበሩ፡፡ ለኔ ያ ትግል ፖለቲካ ውስጥ ከገባሁ በኋላ እንኳን ያላየሁት፣ ሠራተኞቼንና ድርጅቱን ለማዳን ያደረግሁት ትልቅ ትግል ነበር፡፡ የምሁራንን ተሳትፎ በገለፁበት የመፅሃፍዎ ክፍል ላይ ምሁራን ወደ መአህድ እንዲቀላቀሉ ስጠይቅ፣ “ሃይሉ ይዘልፈናል፣ ይንቀናል ይላሉ እንጂ ምንም የረባ ነገር ሲያደርጉ አላየሁም” ብለዋል፡፡

በ97 ምርጫ ቅንጅትን በተመለከተ ነገሮች የተበላሹት ኢንጂነር ግትር ስለሆኑ ነው የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ እርስዎ ምን ይላሉ? እነሱ ምን እንደሚፈልጉ አላውቅም፡፡ በእነሱ ቋንቋ ግትርነት ምን እንደሆነ አላውቅም፡፡ ኢትዮጵያዊነት ግትርነት ከሆነ፣ አዎ ግትር ነኝ፡፡ እነሱ በየኤምባሲው እጅ መንሳት፣እነሱን ተለማምጦ መኖር ትክክለኛ ፖለቲካ ነው ይላሉ፡፡ እነሱ በኛ ፖለቲካ ምን አገባቸው? የኢትዮጵያን ጉዳይ መወሰን ያለብን እኛው ነን፡፡ በእንግሊዝ፣ በአሜሪካ፣ በወልደሀና በምን የሚወሰን ሊሆን አይገባም፡፡ ችግር ሲኖር ሮጠው ለነሱ ይነግራሉ፡፡ መጨረሻ ላይ የኛን ምርጫ ዜሮ አድርጐ ድምፃችንን ለመንግስት የሰጠው ማን ሆኖ ነው? ለአገሩ የሚያስብ እንዲኖር አይፈልጉም። ግትርነት ኢትዮጵያዊነት ከሆነ ልክ ነው፡፡ በመጽሐፍዎ ላይ “ፕሮፌሰር መስፍን መኢአድ ላይ ይዶልታሉ” ብለዋል፡፡ ምን ለማለት ፈልገው ነው? አንዳንድ ሰው ተፈጥሮው ዶላች ነው፡፡ አንዲት አፓርትመንት ዛሬም አለች፤ ኤንሪኮ በታች፡፡ እዛ ቤት የሚዶለተው ዱለታ ዛሬም ብዙ ነው፡፡ ትናንትም በጣም ብዙ ነበር፡፡

ለምን እንደሚዶልት አይገባኝም፡፡ ፕሮፌሰር አስራትን ስለማይወደው ነው… ለምንድነው የማይወዷቸው? እሱን ሄደሽ ብትጠይቂው --- መአህድን ከዛ አውጥቶ ህብረ ብሔራዊ አድርጌያለሁ ብሎ ሌላ ፓርቲ እንዲመሠረት አደረገ፡፡ ከዛ እየደጋገመ ነው ይህን ስራ የሰራው፡፡ መአህድ ከበድ ሲልበት መኢአድን ማዳከም አለብኝ አለ፡፡ ይቅርታ አድርጊልኝና እሱ ለማን እንደሚሠራም አላውቅም፡፡ አንድ ጊዜ ከኢዴፓ ጋር ላስታርቅ አለ፡፡ እነ ልደቱን እናውቃቸዋለን፤ እነሱም ያውቁናል አልኩ፡፡ ግን ቅንጅት ምስረታ ላይ ለእነልደቱ የኃይሉን ቦታ እሰጣለሁ ብለው ማግባባታቸውን ልደቱ ራሱ ሲናገር፣ ፕሮፌሰር መስፍንና ዶ/ር ብርሃኑ፣ እምነት የለ ክህደት የለ ፈጠው ቁጭ አሉ፡፡ እኔ ነገሩን ድሮ አውቄዋለሁ፡፡ አበሻ ሰባቂ ነው፡፡ ሚስጥር አያውቅም፡፡ ሁሉንም ሰምቼ ነበር፡፡ መኢአድ እና ኢዴአፓ- መድህን ውህደት ለመፍጠር ሞክረው ሳይሳካ ወዲያው ሁለቱ ፓርቲዎች በቅንጅት ጥላ ስር በጥምረት ብሎም ለመዋሀድ ተስማምተው ነበር፡፡ ችኮላውን ምን አመጣው? አዎ ችኮላዋን ያመጣው ምርጫ ዘጠና ሰባት ነው።

ተበታትነን ከመቆየት ተባብሮ መሞከሩ ይሻላል ብለን ነው፡፡ የመጀመርያው ላይ እነ ፕሮፌሰር መስፍን ሽማግሌ ነበሩ፡፡ የቅንጅቱ ጊዜ ግን የፓርቲ አባል ስለሆኑ የሚመጣውን መቀበል ይችላሉ በሚል ነበር፡፡ “ኢዴፓ ጥንካሬው አዲስ አበባ ነው፣ መኢአድ ደግሞ ገጠር እንጂ አዲስ አበባ ላይ ጠንካራ አልነበረም፤ ምክንያቱም እኛ አፈቅቤ አይደለንም” ሲሉ ምን ማለትዎ ነው ነው? እኛ ህዝብን አንዋሽም፤ አንዳንዶች ጥሩ ፖለቲካ አይደለም ይሉናል፡፡ መንግስት መሆን በጣም ከባድ ሃላፊነት ነው፡፡ እዳ ነው፤ ህዝብ የሰጠህን መልስ ይልሃል፡፡ ሰውን አስተባብሮ ማምጣት ከባድ ነው፤ አንዳንዱ ካድሬ ሆኖ መለፍለፍና ሚኒስትርነት አንድ ይመስለዋል፡፡ ይሄን ለመግለፅ ፈልጌ ነው፡፡ ተቃዋሚው ውስጥም ከዘረኝነት ጋር የተያያዘ ጉዳይ አንስተዋል፡፡ ችግሩ አለ ማለት ነው? አለ፡፡ አሁንም ያሉ ሰዎች አሉ፤ አንድ ለውጥ ቢመጣ የኔ ቦታ የት ነው የሚሉ፡፡ ሰው በፖለቲካ ሲደራጅ ከታች ነው፤ አንድ ላይ የሚመራረጡት ይተዋወቃሉ፡፡ ከፍተኛ ደረጃ ሲደረስ ያስቸግራል፡፡ እኔ ደቡብ ብዙ ቦታ ሄጃለሁ። ህዝቡ ላዕላይ መዋቅር የገባውን አይጠይቅም፡፡ ጊዶሌ በቋንቋ እንኳን አንግባባም፤ ግን እኛ ነን የተመረጥነው። አማራ ክልል ቀላል ይሆንላቸዋል ብላችሁ ታስቡ ይሆናል፡፡

እጅግ በጣም ከባድ ነው፡፡ አንድ ጊዜ ደቡብ ጐንደር ሄደን በዓይነ ቁራኛ ያዩናል፡፡ ይከታተሉናል። አርብ ቀን ስለሆነ ምን ይበላሉ፤ ምን ይጠጣሉ ብለው ነው፡፡ የከተማ ልጆችን አስጠነቀቅሁ፤ ማታ እራት ጠሩንና ሄድን፡፡ ምግብ ቀርቦ መፋጠጥ ሆነ፡፡ አይበሉም፣ አይናገሩም፤ ከዛ ገባኝ፤ አንድ ቄስ ነበሩና “አባ እባክዎት ይባርኩልን” ስል ሚስጥሩ ተፈታ፤ አለቀ፡፡ በኋላ ስሰማ አዲስ ሃይማኖት ይዘው መጥተዋል ተብሎ ተነግሯቸዋል፡፡ ከዛ ወዲህ ችግር ገጥሞን አያውቅም፡፡ ባህርዳርም ስብሰባ ልናደርግ ሄደን፣ ወያኔ ገበሬዎችን አዘጋጅቶ ጠበቀን፡፡ እኛ ስንገባ ሰው ሁሉ ሲያጨበጭብ፣ አንዱ ቡድን ጭጭ አለ፡፡ አንድ ችግር አለ ብዬ ጠረጠርኩ፡፡ እኛ ጀመርን፣ ሲሰሙ ቆዩና፣ ማጨብጨብ ጀመሩ፡፡ ይሄኔ ካድሬው ጥሎ ሄደና ህዝቡ ራሱ ወሰነ፡፡ የቅንጅት ታሳሪዎች የይቅርታ ይደረግልን ሃሳብ የመጣው ከኛው ውስጥ ነው ብለዋል፡፡ እስቲ ስለእሱ ደግሞ ያጫውቱኝ --- ለምን እንደታሰሩ የረሱት መሰለኝ፤ ብዙ ሰዎች መውጣት ይፈልጉ ነበር፡፡ እኛ የገባነው ትክክል ነን ብለን ነው፡፡ እስር ቤት ሳንገባም በፊት በድብቅ ኤምባሲ ይሄዳሉ፡፡ እኔ አውቅ ነበር፡፡ ከገባን በኋላ የመጨረሻው ውሳኔ እስከዛሬ ይመረኛል፤ ፈረንጅ ምን ይላል - It leaves the bad taste in my mouth፡፡

እነ ፕሮፌሰር እኛ ጋ ይመጣሉ፤ የኛን ይወስዳሉ። ከነሱ ምንም የለም፤ ያው ከእኛም ከሽማግሌዎቹ ጋር የሚሄዱ መጡ፡፡ የኛ አቋም እየሞተ፣ እኛ በመደራደር ፈንታ ከእኛው የእንፈታ ጥያቄ መጣ፡፡ መቼም የማልረሳው ነው፡፡ እኛ እስር ቤት ሆነን መንግስት ፈረንጆቹን ከራሱ ጐን አሰልፏል፡፡ እኛ ተከፋፍለናል፡፡ ምናልባት በፖለቲካ የኔ አቋም የሞኝ ሊሆን ይችላል፡፡ ከቅንጅት ፓርቲ ጋር በተያያዘ የኔ ስህተት ነው ብለው የሚያነሱት ነገር አለ? ቅንጅት በቅንጅትነቱ ቢቀጥል ጥሩ ነበር፤ የኔ ስህተት ምንድን ነው ውህደቱ ነው፡፡ በደንብ ሳንተዋወቅ ወደ ውህደት መግባታችን ነው ስህተቱ፡፡ ከእስር ቤት ከተፈታችሁ በኋላ በኛ ጋዜጣም ተዘግቦ ነበር፡፡ የአሜሪካን ኤምባሲ ቪዛ ከልክሎዎት ነበር፡፡ መጽሐፉ ላይ ያስከለከለኝ ዶ/ር ብርሃኑ ነው ብለዋል---- ተዶልቷል፡፡ እስር ቤት ሆነን ነው ውጪ ካሉት ጋር መነጋገር የጀመሩት፡፡ አንድ ቀን ስናወራ፣ “ስንወጣ ቅንጅትን በአለም አቀፍ ደረጃ እናቋቁማለን” አለኝ “መቼ ነው የምትወጡት?” ስል “እንወጣለን” አለኝ፡፡ ህዝቡስ? ስል ዝም፡፡ ለኔ ይህ አይዋጥልኝም፡፡ ሞትም ከመጣ አብረን እንሞታለን አልኩ፡፡ ይሄኔ በአቋም ተለያየን። በኋላም መኢአድ እንደአንጋፋነቱ ሳይሆን ተመልካች ሆነ፡፡ ቅንጅቱን ስንመሰርት እኮ ቀስተደመና ምንም አባል አልነበረውም፡፡ ኢድሊን እርሺው፤ ፈቃድ ብቻ እንጂ ከጀርባ ምንም የለም፡፡ ችግሩ የመጣው ትልቁ የቅንጅት ፖርቲ መኢአድ ስለሆነ የጠቅላይ ሚ/ርነቱን ቦታ ሊወስድ ነው በሚል ነው፡፡ መጀመሪያ አናሸንፍም በሚል ዝም ብለው ነበር፤ ስናሸንፍ ነው ችግሩ ፈጦ የወጣው፡፡ ኢዴፓ ከመኢአድ ስለወጣ የሌጂትሜሲ ጥያቄ ነበረነበት። ቀስተደመና ደግሞ መኢአድን ማመን አልቻለም፤ እኛ ማንም ቢመጣ ተስማምተን ነበር፡፡

ስልጣኑ ቢመጣም ለማስመሰል አንድ አመት እቆይ ይሆናል እንጂ እለቃለሁ ብያለሁ፤ ግን ያለመተማመን ነበር፡፡ አሁን መኢአድ በምን ሁኔታ ላይ ነው? 97 ላይ የነበረው ጥንካሬ አሁን የለውም፡፡ በጣም ተዘምቶባታል፡፡ ኢህአዴግ በውስጥ ሪፖርቱ መኢአድ አልጠፋ ብሎናል ብሏል፡፡ ቀስ በቀስ ለማገገም እየሰራን ነው፡፡ መኢአድ የደከመው ውጪ አገር የነበረው የገንዘብ ምንጫችን በተለያዩ ቅስቀሳዎች በመቋረጡ ነው፡፡ በተቃዋሚ ጐራ ያለውን ፖለቲካ እንዴት ይገመግሙታል? ይቅርታ፤ ምንም የጠለቀ ነገር የለም፡፡ እያንዳንዱን ፓርቲ በደንብ ስታይው ምንም የለውም፡፡ ለሰው ለማሳየት ከሆነ እያንዳንዱ ፓርቲ ውስጥ ማን ነው ያደራጀው? መሪዎቹ ማን ናቸው? የት ነበሩ? የሚለው ጉዳይ ሳይመረመር ጥምረትና ህብረት የሚለው አይሰራም፡፡ ከዚህ በፊት የሠራነው ስህተት ይበቃል፡፡ ደህና ተቃዋሚን ለመፍጠር ከልብ ከሆነ ጊዜ አይፈጅም፡፡ መኢአድ ከድሮው የደከመ ቢሆንም አሁን ካሉት ጋር ሲታይ እንደሱ መሠረት ያለው የለም፤ እኔ አንገቴን እሰጣለሁ፡፡ እኛ መጮህ መፎከር ባህላችን አይደለም፡፡ በቅርቡ ጥንካሬውን ይመልሳል፤ እኔም የወጣሁት ፓርቲው መስራት ያለበት በኔ ፍጥነት አይደለም፤ በወጣት ጉልበት ነው በሚል ነው፡፡

ሙዚቃ እወዳለሁ፤ አንጐራጉር ነበር ብለዋል፡፡ ስለሙዚቃ ዝንባሌዎ ይንገሩኝ አንጐራጉር አትበይኝ እንጂ እነግርሻለሁ፡፡ ሙዚቃ ከድሮም በጣም እወዳለሁ፡፡ አሜሪካን አገር ምህንድስና ለመማር ሄጄ፣ የየዶርሚተሪው ቡድን አለ፡፡ እኔን ሀሪ ቤላፎንቴን ይሉኝ ነበር፡፡ አንድ ጊዜ ዴንቨር መንገድ ላይ ስሄድ አንድ የሙዚቃ ትምህርት ቤት አየሁ፡፡ ለምን አልማርም ብዬ ገባሁ፡፡ ያነጋገረችኝ ሴት “ምን ያህል ጊዜ ትቆያለህ?” አለችኝ፡፡ ሶስት ሳምንት አልኳት፤“ብዙ ባይሆንም ናና ተማር” አለችኝ፤ ገባሁ፡፡ ቀን ቀን የግድብ ዲዛይን እሰራለሁ፤ ማታ ማታ ሙዚቃ (ፒያኖ) እማራለሁ፡፡ በኋላ ልሄድ ነው ስላት “እንዴት ታቆማለህ?” ብላ ዲትሮይት ፌላርሞኒክ ለሚባል ተቋም ደብዳቤ በመፃፍ “መማር አለብህ፤ተሰጥኦ አለህ” አለችኝ፤ እሷ መሀንዲስ እንደሆንኩ አላወቀችም፡፡ አገሬ ስመጣ ደግሞ ቤተሰቤን ላበሳጭ እንዴ ብዬ ዝም አልኳት፡፡ ከተቋሙ በየቀኑ እየደወሉ “አትመጣም?” ይሉኝ ነበር፤ በኋላ ሠለቻቸውና ተውኝ፡፡

የማንን ሙዚቃ ነው የሚወዱት? ሁሉንም እወዳለሁ፡፡ ግድየለሽም--- በኋላ ስም ጠርቼ ልኮራረፍ ነው፡፡ የእነቻኮቭስኪን ሙዚቃ፣ የጣሊያን ዘፈኖች እወድ ነበር፡፡ በኋላ አማርኛ እየጣፈጠኝ መጣ። በእንግሊዝኛ መልክ የሚዘፈነው ብዙ አይመስጠኝም። It does not send me ይላል ፈረንጅ፡፡ እነ ቴዲ፣ መሐሙድ፣ ነፍሱን ይማርና ጥላሁን ገሰሰ፣ ብዙነሽን እወድ ነበር፡፡ አሁንም ቢሆን አልዘፍንም እንጂ ሰው ሲዘፍን ለማየት የትም እገባለሁ፡፡ ኮሌጅ እያሉ እግር ኳስ ይጫወቱ ነበር፡፡ ስንት ቁጥር ነበር የሚጫወቱት? አምስት ቁጥር፡፡ ቁመቴ ረጅም ስለሆነ ስዊዲናዊው አሰልጣኛችን ሩጫና ረጅም ዝላይ ያሠራኝ ነበር፡፡ በዛን ጊዜ ፉክክርም አልነበረም፡፡ ሌላ ደግሞ በእግር መሄድ እወዳለሁ፡፡ የዛሬን አያድርገውና ጀሞ ሄጄ ብረት አነሳ ነበር፡፡ ኢኒጂነር ሃይሉ የሚወዱት ምግብና መጠጥ ምንድነው? ሰው ጠጅ ይላል አይደል፤ እኔ ጠላ ነው የምወደው። አሁን ዳያቤቲክ ስለሆንኩ ሳላውቀው ጥሩ ነገር ነው የመረጥኩት፡፡ ከምግብ የጣሊያንና የፈረንሳይ ምግብ እወዳለሁ፡፡ ከእኛ ደግሞ ገጠር ስሄድ ጥብስ እና ሚጥሚጣ ነው የምወደው፡፡ ልጆቼ በአገራቸው ባህል ባለማደጋቸው ቅሬታ አለኝ ብለዋል--- ሶስቱ ልጆቼ በጣም ትንሽ ሆነው ነው ወደ ውጪ የሄዱት፡፡ የኔ ትኩረት እነሱ ላይ አልነበረም፡፡ አንድ አባት ለልጆቹ ያን ትኩረት ካልሰጠ ቅር ይለዋል፡፡ የኔ አባት እስከሚሞት ድረስ ትኩረት ሰጥቶኛል፡፡

እኔ ያን ለልጆቼ አልሰጠሁም፤ በዚህ ይቆጨኛል፡፡ ትልቅ ለውጥ አመጣለሁ ብዬ አይደለም፡፡ ወጣት በወጣትነት መንገዱ ይሄዳል፡፡ አማራጮች እንዳሉ የማሳየት፣ እኔ ምን አይነት ዲሲፕሊን ኖሮኝ እንዳደግሁ እንዲያውቁ የማድረግ ነገር ነው፡፡ ወንዶቹን ደርግ ወታደር ውስጥ ይከታቸዋል በሚል ስጋት ያለጊዜያቸው ከኢትዮጵያ አስወጣኋቸው። ጓደኞቻቸው ተገድለዋል፤ ብዙዎች ታስረዋል፤ በኋላ ሳስበው ቀውጢ ጊዜ ባይሆን ኖሮ ልጆቼ ምን አይነት ልጆች ይሆኑ ነበር እላለሁ፡፡ አባቴ ትምህርት ሳይሆን ፍቅር ሰጥቶኛል፡፡ የኔ ልጅ ከኔ መማር ነበረባቸው ብዬ ይቆጨኛል፡፡ ሌላ መጽሐፍ እየፃፉ ነው፡፡ ከአሁኑ በምን ይለያል? አሁን የወጣው ተከታይ ክፍል አለው፡፡ በእንግሊዝኛ ዝርዝሮች የተካተቱበት መጽሐፍ አወጣለሁ፡፡ ያው እንደምታይው ከእስር ቤት ቅርስ አንዱ ህመም ነው፡፡ ቀጥ ብዬ መሄድ አልችልም፤ ህክምናዬን ጨርሼ ስመጣ መጽሐፉ ይደርሳል ብዬ አስባለሁ፡፡

                በሁለት ዙር ምርጫ ለ12 አመታት ስልጣን ላይ የቆዩት ፕሬዚዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ የሚገባቸውን ያህል አልሰሩም በማለት ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተናገሩ ሲሆን አማካሪያቸው አቶ አሰፋ ከሲቶ እና የፓርላማ የግል ተመራጭ ዶ/ር አሸብር በበኩላቸው፤ ፕሬዚዳንቱ ውጤታማና እድለኛ እንደሆኑ ገለፁ፡፡ “ፕሬዚዳንቱ ይህን ሰሩ የምለው ነገር የለም፣ ቦታው በራሱ የሚሰጠው የስራ ሃላፊነት እዚህ ግባ የሚባል አይደለም” ያሉት ዶ/ር ያዕቆብ ሃ/ማርያም፤ “ፕሬዚዳንቱ በግላቸው መስራት የሚችሉት በርካታ ስራ ቢኖርም አንዱንም አላየንም” ብለዋል፡፡ የኢዴፓ ሊቀመንበር አቶ ሙሼ ሰሙ በበኩላቸው፤ “ፕሬዚዳንት ግርማ በተለይ ለሁለተኛ ጊዜ መመረጣቸው ፈጽሞ ስህተት ነበር” ይላሉ።

በመጀመሪያዎቹ አመታት፣ ፕ/ር ግርማ ህገ-መንግስቱ ከሚፈቅድላቸው ስልጣንና ተግባር በተጨማሪ በርካታ በጐ ስራዎች ላይ እየተሳተፉ ነበር የሚሉት አቶ ሙሼ፤ እየቆየ ግን የሰውየው እድሜና የጤና ሁኔታ ከመስራት አግዷቸዋል ብለዋል። ኢትዮጵያ በበርካታ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ውስጥ የምትገኝ አገር እንደሆነች አቶ ሙሼ ጠቅሰው፤ ፕሬዚዳንቱ ርዕሰ ብሔርነታቸውንና የአገር ምልክትነታቸውን ተጠቅመው መስራት ነበረባቸው ብለዋል፡፡ በፕሬዚዳንቱ የ12 ዓመት የስልጣን ቆይታ አገሪቱን ወደፊትም ሆነ ወደኋላ ያራመድ ጠንካራም ሆነ ደካማም ነገር አላየሁም ብለዋል - አቶ ሙሼ፡፡ በፕሬዚዳንትነታቸው እንኳን አቶ ግርማ ወ/ጊዮርጊስ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳም ምንም አልሰሩም በማለት አስተያየት የሰጡት ፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም፤ ቦታውም እንዲሁ በስም ብቻ እንዲቆይ በህገመንግስቱ የታጠረ ስለሆነ የፕሬዚዳንቱ ተግባር ቤተመንግስት ውስጥ ተቀምጦ ኖሮ ጊዜው ሲደርስ መውጣት ነው ብለዋል፡፡

በፓርላማ ብቸኛ የግል ተመራጭ ዶ/ር አሸብር ወ/ጊዮርጊስ ግን፣ ፕሬዚዳንቱ ህገ-መንግስቱ የሰጣቸውን ስልጣንና ተግባር በአግባቡ ተወጥተዋል ብለው ያምናሉ፡፡ ዶ/ር አሸብር፣ የእኛ አገር መንግስታዊ ስርዓት ፓርላሜንታዊ ስለሆነ ብዙውን የአፈስፃሚነት ስራ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚሰጥ ነው ያሉት ዶ/ር አሸብር፤ ፕሬዚዳንት ግርማ ባልተሰጣቸው ሃላፊነት አልሰሩም ተብለው ሊወቀሱ አይገባም ብለዋል፡፡ “ፕሬዚዳንቱ በህገ-መንግስት የተሰጣቸውን ስልጣንና ተግባር ከመወጣት በተጨማሪ አካባቢንና ተፈጥሮን በመንከባከብም ከፍተኛ ስራ ሰርተዋል” ያሉት ዶ/ር አሸብር፤ ፕ/ት ግርማ ባሳለፏቸው 12 ዓመታት ውጤታማ መሪ ነበሩ ብለዋል፡፡

ፕ/ት ግርማ በግላቸው በተፈጥሮ ሳይንስና በአካባቢ ጥበቃ ላይ ከፍተኛ ፍላጐት እንዳላቸው ቢናገሩም በተግባር ያመጡት ውጤት አላየሁም የሚሉት የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት “በሃይማኖት፣ በፖለቲካና በሰብአዊ መብት ጉዳዮች ዙሪያ ብዙ መስራት ይችሉ ነበር፤ ግን አላደረጉም” ብለዋል፡፡ የፕሬዚዳንት ግርማ አማካሪ አቶ አሰፋ ከሲቶ በበኩላቸው፤ ፕ/ት ግርማ በስልጣን ዘመናቸው ውጤታማና እድለኛ መሪ መሆናቸውን የገለፁ ሲሆን፤ በእውቀታቸው፣ በቋንቋ ችሎታቸው፣ በአንባቢነታቸውና በስራ ሰአት አክባሪነታቸው ወደር የሌላቸውና ለሌሎች አርአያ ሊሆኑ የሚችሉ መሪ ናቸው ሲሉ አድንቀዋቸዋል፡፡

ፕ/ት ግርማ እድለኛ ናቸው ያሉበትንም ምክንያት ሲያስረዱ፤ በእርሳቸው ዘመን ታላቁ የህዳሴ ግድብ መጀመርና የአምስት አመቱ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ውጤታማ ጅምር ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል፡፡ የወደፊቱ ፕሬዚዳንት ማን ይሁን በሚለው ዙሪያ ጥያቄ የቀረበላቸው አብዛኞቹ አስተያየት ሰጪዎች እከሌ ይሁን በሚል ስም ከመጥቀስ የተቆጠቡ ሲሆን ዶ/ር ያዕቆብ ሃ/ማሪያም ብቻ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ም/ቤት ፕሬዚዳንት ወ/ሮ ሙሉ ሰለሞን ቢመረጡ ምኞታቸው እንደሆነ ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

ለህዝብ የሚታየው ፓትሪያርኩ በተገኙበት ነው በየእለቱ ከ3ሺህ ሰው በላይ ቦታውን እየጎበኘ ነው

በአቃቂ ቃሊቲ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስትያን ከሰማይ ወረደ የተባለው መስቀል ፓትርያርኩ በተገኙበት ለህዝብ እንዲታይ መግቢያ መንገድ እስኪሰራ ድረስ የተራዘመ ሲሆን፣ በመስቀሉ ላይ የሳይንስ ምርመራ እንደማይፈቀድ ተገለፀ፡፡ ከሶስት ሳምንት በፊት በፍንዳታ ድምፅና በብርሃናማ ቀስተደመና ከሰማይ ወረደ የተባለው መስቀል፣ በሚቀጥለው ሳምንት መስከረም 19 ቀን ለህዝብ ይታያል ተብሎ የነበረ ቢሆንም፣ ፓትርያርኩ የሚገኙበት ስነስርዓት ለማዘጋጀት ጊዜው እንደተራዘመ የቤተክርስቲያኗ አስተዳዳሪዎች ተናግረዋል፡፡ መስቀሉ ለህዝብ የሚታየው ቅዱስ ፓትሪያርክ አቡነ ማቲያስ በተገኙበት ስነስርዓት መሆን አለበት መባሉን አስተዳዳሪዎች ጠቅሰው፤ መንገዱ ጭቃ ስለሆነ ጠፈፍ ብሎ ለመኪና እስኪስተካከል ድረስ ቀኑ መራዘሙን ገልፀዋል፡፡ ቀኑ ገና እንዳልተወሰነና ለፓትሪያርኩ ጋር ውይይት እየተደረገበት ነው ያሉት የቤተክርስቲያኒቱ አስተዳዳሪዎች፤ ስነስርዓቱን ህዳር 11 ቀን ለማካሄድ እንደታሰበ ጠቁመዋል፡፡

ከአዲስ አበባና በአቅራቢያዋ ከሚገኙ አካባቢዎች በየእለቱ ከ3ሺ በላይ ሰዎች ቦታውን እየጎበኙ መሆናቸውን የገለፁት የቤተክርስቲያኗ መጋቢ ሃዲስ ፍሰሃ፤ እኛም በየእለቱ ከ15 ጊዜ በላይ ስለ ተከሰተው ተዓምር ገለፃ እናደርጋለን ብለዋል፡፡ መስቀሉ ባረፈበት ሳር ላይ እንዲሁም ወደ ቤተ መቅደሱ ከገባ በኋላ የተነሱ ፎቶዎችን የያዘ ካርድ ታትሞ ለምዕመናን በ10 ብር እየተሸጠ ነው፡፡ በፎቶግራፍ ላይ የሚታየው መስቀል በሰው የተሰራ የዕደ ጥበብ ውጤት እንደሚመስል በመጥቀስ ከሰማይ ወረደ መባሉን የሚጠረጥሩ መኖራቸውን በተመለከተ መጋቢ ሃዲስ ፍስሃ፣ እውነቱን የሚያውቀው ፈጣሪ ነው ብለዋል፡፡

በምድራችን የተሰራ የሚመስል መስቀል ከሰማይ ሊወርድ አይችልም የምንል ከሆነ፣ በምድራችን የምናረባው አይነት በግ ለአብርሃም ከሰማይ ወርዶለታል የሚለውን የመፅሃፍ ቅዱስ ቃል መጠራጠር ይሆናል ብለዋል መጋቢ ሃዲስ ፍስሃ፡፡ የመስቀሉን ስሪት እንዲሁም መስቀሉ አረፈበት የተባለውን ሳርና አፈር ለመመርመር ሃሳብ ተነስቶ እንደሆነ ተጠይቀው መጋቢ ሃዲስ ሲመልሱ፤ “ይህ መስቀል የቤተክርስቲያኒቱ የክብር መገለጫ ነው” በማለት ተቃውመዋል፡፡

እስካሁን በስፍራው የተፈፀመውን ተአምር ሰምተው የሚያደንቁ እንጂ በመስቀሉና በቦታው ላይ እንመራመራለን የሚሉ ምሁራን አላጋጠሙኝም ያሉት መጋቢ ሃዲስ፤ “እንዲህ ያለ ጥያቄ ያላቸውም ካሉም፣ የማይሞከር ነው” ያሉት መጋቢ ሃዲስ፤ የሃይማኖት ጉዳይ ስለሆነ ቦታውን እንፈትሻለን፣ የወረደውን መስቀል እንመረምራለን ለሚሉ የሳይንስ ባለሙያዎች ፈፅሞ አይፈቀድም ብለዋል፡፡ መስቀሉ ከሰማይ ከመውረዱ አስቀድሞ ራዕይ ታይቶኛል የሚል ሰው እስካሁን አላጋጠመን ያሉት መጋቢ ሃዲስ፤ ቤተክርስቲያኒቱን ያቋቋሙት አባት ግን፣ ቦታው የእግዚአብሔር ክብር መገለጫ እንደሚሆን በራዕይ እንደታያቸው ተናግረው ነበር ብለዋል፡፡

Published in ዜና

“ህይወቴ እና ለኦሮሞ እና ለሌሎችም የኢትዮጵያ ህዝቦች ያለኝ ራዕይ” በሚል ርዕስ በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተዘጋጀው የአቶ ቡልቻ ደመቅሳ መጽሐፍ በአሜሪካ ታትሞ በውጭ አገራት ለገበያ ቀረበ፡፡ መፅሃፉ አቶ ቡልቻ ከተወለዱባት የቦጂ በርመጂ ወረዳ ጀምሮ ከኦፌዴን ሊቀመንበርነት እስከለቀቁበት ጊዜ ድረስ ያሳለፉትን የትምህርት፣ የስራ እና የፖለቲካ ህይወት ይዳስሳል፡፡ ዘመናዊ ትምህርት ለመማር ያደረጓቸውን እልህ አስጨራሽ ሙከራዎች፣ ከአሜሪካን በኢኮኖሚክስ ተመርቀው ከመጡ በኋላ በገንዘብ ሚኒስቴር ውስጥ በምክትል ሚኒስትር ማዕረግ ባገለገሉባቸው አመታት ያጋጠሟቸውን ውጣ ውረዶች፣ በአለም ባንክ የኢትዮጵያ ተወካይ በመሆን እንዲሁም በዩኤንዲፒ ስለሠሯቸው ስራዎች በመጽሐፋቸው ተርከዋል፡፡

የኦሮሞ ህዝብን ጥያቄ አንስተው በፖለቲካው መስክ ስላደረጉት ተሳትፎ የፃፉት አቶ ቡልቻ፤ አዋሽ ባንክን ለመመስረት ያደረጉትን አስተዋጽኦና በባንኩ ውስጥ የተፈጠረውን አለመግባባትም በስፋት ዳስሰዋል፡፡ መጽሐፉ 180 ገፆች ያሉትና በ20 ምዕራፎች የተከፋፈለ ሲሆን በኦሮሚኛ እና በአማርኛ ቋንቋዎች ተተርጉሞ ለአገር ውስጥ ገበያ እንደሚቀርብ አቶ ቡልቻ ደመቅሳ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

ለወራት በእስር የቆዩት አቶ ተክለአብ ዘርአብሩክ በዋስ ተለቀቁ

የተለያዩ ሃሰተኛ የንግድ ፍቃዶችን በማውጣት፣ ከገቢዎችና ጉምሩክ መስሪያ ቤት ባለስልጣናት ጋር በመመሳጠር ቀረጥና ታክስ ሳይከፍሉ ሸቀጦችን ወደ ሀገር ውስጥ አስገብተዋል እንዲሁም በህገወጥ መንገድ የተገኘን ገንዘብ የራሳቸው አስመስለው ይዘዋል የተባሉ ሁለት ነጋዴዎች በቁጥጥር ስር ውለው በትናንትናው እለት ፍ/ቤት የቀረቡ ሲሆን የ14ቀን የምርመራ ጊዜም ተሰጥቶባቸዋል፡፡ በፌደራሉ የስነምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን በቁጥጥር ስር የዋሉት አቶ ታደለ ብርሃኑ እና አቶ ወ/ሚካኤል ሃለፎም የተባሉት ተጠርጣሪዎች በተለያዩ የንግድ ስራዎች ላይ የተሰማሩ መሆናቸውንና የተጠረጠሩበትን ወንጀል የፈፀሙት ጉዳያቸው በፍ/ቤት እየታየ ካሉት የቀድሞ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ሃላፊዎች ጋር በመመሳጠርና ጉቦ በመቀባበል ነው ተብሏል፡፡

የመርማሪ ቡድኑ እስካሁን በህገ ወጥ መንገድ የተገኘን ንብረት የራስ አድርጐ መጠቀም ከሚለው የወንጀል ፍሬ ጋር በተያያዘ ንብረቶቹ የሚገኙበትን ቦታ ማግኘቱን ለፍ/ቤቱ አመልክቶ፤ ይቀሩኛል ያላቸውን ተግባራትም አስረድቷል፡፡ ከሚቀሩ የምርመራ ስራዎች መካከልም የተጠርጣሪዎችን ቃል መቀበል፣ የተለያዩ የሰነድ ማስረጃዎችን ከሚመለከታቸው መስሪያ ቤቶች ማሰባሰብ እንዲሁም የምስክሮችን ቃል መቀበል ይገኙበታል፡፡

እነዚህን ስራዎች ለማጠናቀቅም የ14 ቀን የምርመራ ጊዜ እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡ ተጠርጣሪዎች በበኩላቸው፤ የየግል ምክንያቶቻቸውን አቅርበው ጉዳያቸውን በዋስ ሆነው እንዲከታተሉ የጠየቁ ቢሆንም ፍ/ቤቱ ጥያቄያቸውን ውድቅ በማድረግ መርማሪ ቡድኑ የጠየቀውን የ14 ቀን ቀጠሮ ፈቅዶ ጉዳዩን ለመስከረም 23 ቀን 2006 ዓ.ም ቀጥሯል፡፡ በሌላ በኩል ዳኞች ተሟልተው ባለመቅረባቸው በፅ/ቤት በኩል በሁለት ዳኞች በተስተናገደው በእለቱ ችሎት ከኦዲት ምርመራ ጋር በተያያዘ ክስ ሳይመሰረትባቸው ጉዳያቸው ወደ ጊዜ ቀጠሮ ከተመለሱት 4 ተጠርጣሪዎች መካከል በባለስልጣን መስሪያ ቤቱ የአዋሽ ቅርንጫፍ ሠራተኛ በነበሩት በአቶ ተክለአብ ዘርአብሩክ ላይ የሚካሄደው ምርመራ በመጠናቀቁ በ20ሺህ ብር ዋስ ተለቀዋል፡፡

በእነ አቶ ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስ መዝገብ ተካተው ጉዳያቸውን ሲከታተሉ የነበሩት አቶ ምህረተ አብ አብርሃ እና አቶ በእግዚአብሔር አለበል ላይ የሚካሄደው የኦዲት ምርመራ ስራ አለመጠናቀቁን ለፍ/ቤቱ ያመለከተው የመርማሪ ቡድኑ፤ ምርመራውን ለማጠናቀቅ ተጨማሪ 14 ቀን የጠየቀ ቢሆንም ፍ/ቤቱ የ8 ቀን ጊዜ ብቻ ለመጨረሻ ጊዜ በመፍቀድ መዝገቡን ለመስከረም 20 ቀን 2006 ዓ.ም ቀጥሯል፡፡ የሌላኛው ተጠርጣሪ የአቶ ፍፁም ገ/መድህን መዝገብ በእለቱ ባለመቅረቡ ጉዳያቸው በአዳሪ እንዲሰማ ብይን ተሰጥቶበት ለሰኞ መስከረም 13 ቀን 2006 ተቀጥሯል።

Published in ዜና

 ሃዘንተኞች ችግር ላይ ወድቀዋል

ምኒሊክ ሆስፒታል ውስጥ በሚገኘው የአገሪቱ ብቸኛ የአስከሬን ምርመራ ላይ ተሰማርተው የቆዩት ኩባዊቷ ሃኪም በመታመማቸው እስኪሻላቸው ድረስ ከሐሙስ ጀምሮ አገልግሎቱ ተቋረጠ፡፡ በሆስፒታሉ አገልግሎት ለማግኘት የሄዱ የሟች ቤተሰቦች፤ ሆስፒታሉ አስቀድሞ ባለሙያ ባለማዘጋጀቱ ለእንግልት ዳርጐናል ብለዋል፡፡ በመኪና አደጋ ወንድሙ ያረፈበት ሙሉጌታ ኩሳ፤ ከጥቁር አንበሳ የተላከውን የወንድሙን አስከሬን ለመረከብና ለቀብር ወደ ትውልድ ሀገሩ ወደ ወለጋ ለመውሰድ ነበር ወደ ምኒልክ ሆስፒታል ያመራው፡፡

የአስከሬን ምርመራ ላልተወሰነ ጊዜ ተቋርጧል የሚል ማስታወቂያ ተለጥፎ ሲያይ ግራ እንደተጋባ የሚገልፀው ሙሉጌታ፤ ሃላፊዎችን ባነጋግርም መፍትሔ አልሆነኝም ብሏል፡፡ ባለሙያዋ ሃኪም በህመም ምክንያት በስራ ገበታቸው ላይ ሊገኙ አልቻሉም ተብያለሁ ያለው ሙሉጌታ፤ “አገልግሎቱ መቼ እንደሚቀጥል እንኳ አይታወቅም፣ ግራ ገብቶኛል” ብሏል፡፡ ለመቅበር እድር ያስነገሩ፣ ወደ ክፍለሀገር ለመውሰድ የተዘጋጁ፣ መኪና ተከራይተው አስከሬኖችን ለመረከብ የመጡ በርካታ ቤተሰቦች፤ በሃዘን ላይ መላ የሌለው እንግልት ተጨምሮባቸው ተቸግረዋል፡፡

የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የግድያ ምርመራ ክፍል በበኩሉ፤ ላለተወሰነ ጊዜ አገልግሎት ተቋርጧል የሚል ማስታወቂያ መለጠፍ ተገቢ አይደለም ብሏል፡፡ ምርመራ ሲስተጓጐል የሟች ቤተሰቦች ይቸገራሉ በማለት የተናገሩት የግድያ ምርመራ ክፍል ባልደረባ፤ ለፖሊስ የምርመራ ስራዎችንም እንደሚያጓትት ለምኒሊክ ሆስፒታል ተናግረናል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያዊ የአስከሬን ምርመራ ባለሙያ እንደሌለን የሚገልፁት የአስከሬን ምርመራ ክፍል ሃላፊ አባ ሃይለማርያም ወርቅአለማሁ፤ ኩባዊቷ ሃኪም እስከ ረቡዕ ድረስ ስራ ላይ ነበሩ ብለዋል፡፡ ሃኪሟ መታመማቸውን ተናገርን እንጂ አገልግሎቱ ተቋርጧል አላልንም በማለት ሃላፊው ቢገልፁም፤ ሌላ አማራጭ አገልግሎት የለም፡፡ ቀድሞውኑ አማራጭ መንገዶች ለምን እንዳልተዘጋጀ ተጠይቀው ሃላፊው ሲመልሱ፣ በአገራችን የአስከሬን ምርመራ ባለሙያ ባለመኖሩ ሳቢያ የተፈጠረ ችግር ነው፤ ተጨማሪ ባለሙያዎችን ከኩባ ለማስመጣት ሁሉንም ነገር ጨርሰናል ብለዋል፡፡

አገልግሎቱ መቼ እንደሚቀጥል ሳይለገጽ “ላልተወሰነ ጊዜ” ተብሎ በማስታወቂያ መለጠፉን በተመለከተ ተጠይቀውም፤ ቀን ወስነን ብንጽፍና በተባለው ጊዜ ሀኪሟ ባይመጡ ከባለጉዳይ ጋር ችግር ውስጥ ልንገባ እንችላለን በማለት መልሰዋል፡፡ በሆስፒታሉ በቂ የአስከሬን ማቆየያ ስፍራ በመኖሩ የሚመጡትን አስከሬኖችን ተቀብለን የታመሙት ሃኪም ሲመጡ ስራቸውን እንደሚጀምሩ ሃላፊው ገልፀው፤ አስክሬኑ ላይ የሚመጣ ለውጥም ሆነ ችግር አይኖርም ብለዋል። ኩባዊቷ ሃኪም ለሁለት ዓመት ኮንትራት የመጡ ሲሆን አንድ አመት በረዳትነት ሲሰሩ ቆይተው ከዚያ ወዲህ በብቸኝነት መስራት መጀመራቸው ታውቋል፡፡

Published in ዜና

            ሰማያዊ ፓርቲ ነገ እሁድ በመስቀል አደባባይ የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ እንቅፋት እንዳጋጠመው የተናገሩት የፓርቲው ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት፤ ቦታው ለተቃዋሚዎች አይፈቀድም እንደተባሉ ገለፁ፡፡ በአዲስ አበባ መስተዳድር፣ የስብሰባና ሰላማዊ ሰልፍ ማሳወቂያ ክፍል ሃላፊ አቶ ማርቆስ ብዙነህ በበኩላቸው፤ ስፍራው ለልማት የታጠረ በመሆኑ የትኛውም አካል በስፍራው ሰላማዊ ሰልፍ እንዲያካሂድ አይፈቀድለትም ብለዋል፡፡ ሰላማዊ ሰልፉን በጃንሜዳ እንዲያካሂዱ ሃሳብ አቅርበንላቸዋል ይሉት አቶ ማርቆስ፤ “በዚህ ካልተስማሙ አማራጭ ቦታ እንዲያቀርቡ በደብዳቤ አሳውቀናቸዋል” ብለዋል፡፡ በመስቀል አደባባይ ሰላማዊ ሰልፍ እንደምናካሂድ ለመስተዳድሩ በደብዳቤ ያሳወቅነው ከ10 ቀን በፊት ነው የሚሉት ኢ/ር ይልቃል በበኩላቸው፤ መስተዳድሩ ቅሬታውን በ12 ሰዓት ውስጥ ካልገለፀ እንደተስማማ ስለሚቆጠር ፅሁፎችን አትመን ስናሰራጭ፣ በሚዲያ በይፋ ስናስተዋውቅ ቆይተናል፤ ስለዚህ በዚያው እንቀጥላለን ብለዋል፡፡

ጃንሜዳ በክረምቱ ዝናብ በሙጃና በጭቃ ስለተሸፈነ ለሰላማዊ ሰልፍ አያመችም ይላሉ፡፡ ቦታው ለተቃዋሚዎች አይፈቀድም ተብለናል የሚሉት ኢ/ር ይልቃል፤ ለልማት ታጥሯል መባሉም ተቀባይነት እንደሌለው ሲናገሩ፤ ቦታው ከጥቂት ቀናት በኋላ የደመራ በዓል ይካሄድበታል፤ ክልከላው “እኛን ለማዳከም የታሰበ ስራ ቢሆንም ትግላችንን እንቀጥላለን” ብለዋል፡፡

የመስቀል በዓልን አከባበር በተመለከተ ጥያቄ ያቀረብንላቸው አቶ ማርቆስ፣ “የመስቀል በዓል ብሔራዊ እና ሃይማኖታዊ በዓል በመሆኑ፣ እኛ መፍቀድም መከልከልም አንችልም” ብለዋል፡፡ ኢህአዴግስ ሠልፍ በስፍራው ማካሄድ ይችላል ወይ ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ፣ “ጉዳዩ የገዢ ፓርቲ ወይም የተቃዋሚ ፓርቲ የሚል አይደለም፤ ስፍራው በከፍተኛ በጀት በውጭ ኮንትራክተሮች እየለማ ስለሆነ፣ የትኛውም አካል ሰላማዊ ሰልፍ ማካሄድ አይችልም” ብለዋል፡፡ ሰማያዊ ፓርቲም ጃንሜዳ አይመቸኝም የሚል ከሆነ አማራጭ ቦታ ያቅርብና አስተዳደሩ ተወያይቶ ይወሰናል በሚል ሃሳባችንን በደብዳቤ ገልፀናል ብለዋል - አቶ ማርቆስ፡፡

Published in ዜና
Page 6 of 16